Monday, 31 March 2014 11:07

የጥንቱ አገረሸ

ሁሉን የሚችል ዳስ አንጣሎ፤ ገትሮ
ደልድሎ፤ አሳምሮ
ሊጡ ተቦካና እንጀራው ተጋግሮ
ለብሶ ተከምሮ፤
ጠጁ ተጣለና በጠላ ጉሮሮ
ሊወርድ ተደርድሮ፤
ወጡ በያይነቱ ባዋቂ ተሠርቶ፤
ቁርጡ ተሰናድቶ፤
ሰው ሁሉ ለመብላት፤ ለመጠጣት ጓጉቶ፤
ሲጠብቅ ሰንብቶ፤
አዝማሪው ለዘፈን ቆሞ ተዘጋጅቶ፤
ማሲንቆው ተቀኝቶ፤

ጨዋታ ፈረሰ!
ዳቦ ተቆረሰ!
ሙሽራው ጠፋና ሠርጉ ተበላሸ፤
የተጠራው ሸሸ፤
ጊዜ ከዳውና በጊዜው ላመሸ፤
ዳሱ ተረበሸ፤
የጥንቱ አገረሸ፡፡
(ከፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም
“ዛሬም እንጉርጉሮ” የተሰኘ የግጥም መድበል የተወሰደ)

Published in የግጥም ጥግ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…ዘንድሮ ብሶት የማይሰማበት፣ አቤቱታ የሌለበት፣ ችግር የማይነገርበት ቦታ ማግኘት አስቸጋሪ እየሆነ ነው፡፡ ነገሮች ለምን በሦስትና በአራት እጥፍ ፍጥነት እየባሰባቸው እንደሚሄዱ ወደ እንቆቅልሽነት እየተቃረበብን ነው። ዓመት አልፎ ዓመት በመጣ ቁጥር “ከተከታዩ ዓመት ይሻላል…” ከማለት አዙሪት መውጣት አለመቻላችን አይገርማችሁም!
አልናገር ችዬም አልናር
የዘመኑን የዘንድሮን ነገር፣
ከመጨነቅ ከመጠበብ በቀር
ያገኘሁት የለም ሌላ ነገር፣
ተብሎ ከዓመታት በፊት የተዘፈነው ልክ ላለንበት ዘመን ሳናውቀው የከረመ ንግርት ቢጤ ይመስላል፡፡
እናላችሁ… በህትመት ሆነ በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ከምናነባቸውና ከምንሰማቸው ነገሮች አብዛኞቹ የተለያዩ ችገሮች ናቸው.፡ ሰዋችን እኮ በሚዲያ በኩል… “ኽረ የአገር ያለህ…” የሚለው “ችግርህን አዋየኝ…” የሚለው ሰሚ ሲያጣ፣ “ምነው የአገሬ ልጅ ከፋህሳ!” የሚል አቃፊ ደጋፊ ሲያጣ ነው። እሱን ሊያገለገሉ የተቀመጡት ከ‘እነመፈጠሩም’ ሲረሱት ባገኛት ቀዳዳ…
ጩኸቴን ብትሰሙኝ
ይኸው አቤት አቤት እላለሁ
በደል ደርሶብኝ እጮሀለሁ፣
እያለ ነው፡፡ ሰዋችን…
መሳቁን ይስቃል ጥርሴ መች አረፈ
ልቤ ነው በጣሙን እጅግ ያኮረፈ፣
እያለ ነው፡፡ ይህንን መገንዘብ አሪፍ ነው፡፡ “የምስቀው ለማህበራዊ ኑሮ ብዬ ነው እንጂ ልቤ ቆስሏል…” እያለ ሰሚ ጆሮ ምነው ጠፋሳ!  
እናማ…አስቸጋሪ ጊዜ ውስጥ ነን፡፡ ብዙ ነገሮች ከሀዲዳቸው እየለቀቁ የሄዱ ይመስላል፡፡ “ኸረ በቡሩ ሀዲዱን ስቷል፣ ወዳልተሰፈረንበት እየወሰደን ነው…” ሲባል ነገሬ ብሎ የሚሰማ ጠፍቷል፡፡
ከውሀ ብጠጋ ባሀሩ ነጠፈ
ከዛፉ ብጠጋ ቅጠሉ ረገፈ
እንደምንም ብሎ ይሄስ ቀን ባለፈ፣
ተብሏል፡፡ እና አሁንም የሚይዝ የሚጨብጠው ጠፍቶበት፣ ሁሉም ነገር ጫፏን እንኳን መያዝ እያቃተው፣ በሄደበት አቅጣጫ ችግር አድፈጦ እየጠበቀው… አለ አይደል… “እንደ ምንም ብሎ ይሄስ ቀን ባለፈ…” እያለ ነው፡፡ እናማ…ሰዋችን ይሄን ያህል እየተማረረ ምነዋ ሰሚ ጠፋሳ!
የምር ግን እንግዲህ ጨዋታም አይደል…ስንቱ ሰው አገር ቆርጦ የሚሄደው፣ በመርከብና በጫካ ከአውሬና ከተፈጥሮ ጋር እየታገለ እትብቱ ለተቀበረባት ምድር ጀርባውን ሰጥቶ እየነጎደ ያለው ሁሉም ‘ስለጠገበ’፣ ‘መሥራት እየቻለ ስለሰነፈ’፣ በሰው አገር ‘የሚጠበቀውን መከራና ስቃይ ስላላወቀ’ ብቻ እንዳልሆነ ልብ ይባልልንማ! በአገሩ ላይ እንደ ‘ባለ አገር’ መታየቱ ሲበቃ፣ ነገሮች ሁሉ ከሁለተኛ ዜግነት በታችም ሲያወርዱት…ሲያደናቅፈው “እኔን…” የሚል፣ ሲወድቅ “አይዞህ” ብሎ ደግፎ የሚያነሳ ሲጠፋና ገድገድ ሲባል ጭራሽ ከኋላ የሚገፋ ሲበዛ…ያላየው አገር ቢናፈቀው ምን ይገርማል!
ወሰወሰው፣ ወንዝ እያሻገረ ወሰወሰው፣ አባይ እንዳፈሩ፣ ወሰወሰው፣ ተበትኖ ቀረ ወሰወሰው፣  በየሰው ሀገሩ፣
ተብሏል፡፡ በየሰዉ አገር ተበትኖ የቀረው የመንከራተት አዚም ስላለበት… “የሀበሻ ልጆች እስከ ሦስተኛው ሺህ ዘመን እንደተንከራተታችሁ ትኖሯታላችሁ…” የሚል ‘ይግባኝ የማይጠየቅበት’ እርግማን ስላለበት አይደለም። ችግር ቢበዛበት ነው። መከራ ቢበዛበት ነው፡፡ ‘ባለ አገርነቱ’ ባይከበርለት ነው፡፡
እናላችሁ… ውሀውም ‘እየነጠፈበት’፣ ቅጠሉም ‘እየረገፈበት’ እንደምንም ብሎ “ይሄስ ቀን ባለፈ…” የሚለው ህዝብ ቁጥሩ እየጨመረ ብቻ ሳይሆን እየተባዛ ነው፡፡ ታዲያላችሁ…ችግሩም ሲበዛ፣ ትከሻመ መሸከም ሲያቅተው፣ ጉልበትም ሲደክም…
ሰዋችን…
ሺህ ዘመን አልኖርም እየተጨቃጨቅሁ
ዛሬስ ሲብስብኝ አመረርኩኝ ጨከንሁ፣
የሚል ደረጃ ላይ ይደርሳል፡፡ ነገርዬው…“ካቃተሽ መዋደዱ ያውልሽ መንገዱ…” ነው፡፡
የተሰጠንን አደራ ያልተወጣን፣ ለምናገለግለው ህዝብ ታማኝ ያልሆንን… “ያውልህ መንገዱ…” መባያችን ጊዜያችን በዓመታት ያለፉ መአት አለን፡፡
እናላችሁ…ህዝባችን ወደፊት እንዴት ‘አፍሪካን እንደምናስከነዳ’… ድፍን ዓለም እንዴት ወደ እኛ እንደሚጎርፍ… በተአምራዊ ግስጋሴ የዓዳም ልጆችን እንዴት “ጉድ!” እንድምናሰኝ … ሲነገረው… አለ አይደል… “የዛሬውስ!” እያለ ነው፡፡  
የምር እኮ ኮሚክ ነገር ነው…መሠረታዊ አገልግሎቶች ማግኘት እያቃተን፣ የባክቴሪያ መፈንጫና ‘ነጻ ግዛት’ የሆነው ጨጓራችን የአሲድ ዶፍ እየዘነበበት…ከዓመት ዓመት በእንቁልልጭ ሊያባብሉን ሲሞክሩ አሪፍ ነገር አይደለም፡፡
ግን እኮ ከተነቃቃን ከረምን! “ማሙሽዬ አሁን ዳቦ ስላላገኘህ አታልቅስ፣ ከነገ ወዲያ ቸኮላት ይገዛለሀል…” አይነት ከዓመት ዓመት በ‘ሪሳይከሊንግ’ የሚቀርብ ማባበያ ቀልብ መሳቡ መቅረቱ ይታወቅልንማ!
እናላችሁ…እዚሀ አገር በርካታ ‘መግለጫ ሰጪዎች’ ሊያወቁ ያልቻሉት ሰዉ ስለ ነገ ቸኮላት ለማሰብ የዛሬውን ዳቦ ማግኘት እንዳለበት ነው፡፡
እንግዲህ…ይሄኔ ነው ‘የሚያስብ አእምሮ’ና ‘የማያስብ ጡንቻ’ የሚለየው፡፡ ‘የማያስብ ጡንቻ’ “ውልፍት በላትና የዶሮ ጠባቂ አደርግሀለሁ!” አይነት ቀረርቶ ውስጥ ይገባል…‘የሚያስብ አእምሮ’ ደግሞ “ለካስ ይሄን ያህል ስህተት ውስጥ ገብቻለሁና፣ ይቅርታ…” ብሎ ያበላሸውን ሊያስተካክል ይሞክራል፡፡
የእውነት መንገድ ተሳስቼ
ተቀጣሁ በእውነት ተመርቼ
እውነት ማሪኝ እላለሁ
ይቅርታ እለምናለሁ፣
እንደተባለው…እውነትን “ማሪኝ” ብለን ይቅርታ መጠየቅ የሚገባን ብዙ ነን፡፡ ‘እውነት’ የሚባለው ነገር…አንጻራዊ በሆነበት ዘመን የፀሐይ በምሠራቅ ወጥቶ በምዕራብ የመግባት እውነት የሚሠራው እኛ እስከፈለግን ብቻ በሆነበት ዘመን…
እውነት ማሪኝ እላለሁ
ይቅርታ እለምናለሁ፣
የማለት ድፍረቱን አንድዬ ይስጠንማ!
እናላችሁ…ይሄ የችግርና የብሶት አዙሪት የሆነ ቦታ ላይ ቆሞ፣ ያዘመመው ሁሉ ተቃንቶ፣ የደከመው ሁሉ ተጠናክሮ… አለ አይደል…
ምነው ምነው የአገሬ ልጅ ምነው
ምነው ምነው የእናቴ ልጅ ምነው፣
ወገን መሀል ባይበላስ ምነው
ፍቅር ካለ ትንፋሽም ቀለብ ነው፣
የሚባልባት አገር እንድትሆን… የሚባልለት ዘመን እንዲመጣ እየናፈቅን ነው፡፡
እማሆይ፣ እማሆይ፣ እማሆይ
ፀሎትሽ ተሰማልሽ ወይ
እማሆይ፣ እማሆይ፣ እማሆይ
ስለትሽ ሰመረልሽ ወይ፣
ሲባል… አለ አይደል… አገርም “አዎ ፀሎቴ ተሰምቶለኛል…” “አዎ ስለቴ ሰመሮልኛል…” የምትልበትን ጊዜ እንናፈቃለን፡፡
አባቶቻችን “የሞኝ እጁን እባብ ሁለት ጊዜ ነከሰው፣ አንዴ ሳያይ ሁለተኛ ሲያሳይ” የሚሏት ነገር አለች፡፡ እናማ ሰዋችን አንዴ ‘ሳያይ’ ተነክሶ ይሆናል። ግንላችሁ…‘እያሳየ’ የሚነከስ ሞኝ አለመሆኑን መገንዘብ አሪፍ ነው፡፡ ነገርዬው…
መሳቁን ይስቃል ጥርሴ መች አረፈ
ልቤ ነው በጣሙን እጅግ ያኮረፈ፣
ነው፡፡ ህዝባችን ‘ልቡ በጣም ማኩረፉን’ ማወቁ፣ ጨጓሯው መቁሰሉን መገንዘቡ…
አንተም ላትበጀኝ፣ እኔም ላልበጅህ
አትድረስብኝ፣ አልደርስም ደጅህ
በምንም ነገር አትደልለኝም
እኔን አታስብ አታገኘኝም፣
ብሎ እስከወዲያኛው ‘ከመቆራራጥ’ ያድናል፡፡ ልብ ያለው ልብ ይበል፡፡ (ዛሬ ‘ስነዘፍን’ ዋልናትሳ!)
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

የአሜሪካ መንግሥት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጅነር ይልቃል ጌትነት መርጦ ለመሸለም ጥሪ ማድረጉን የፓርቲው ልሳን ጋዜጣ ባለፈው ሳምንት ዘግቧል፡፡ በሌላ በኩል ከአሜሪካ ኤምባሲ በኩል የተገኙ መረጃዎች የሰማያዊ ፓርቲ መሪ የተመረጡት የአሜሪካ  ስቴት ዲፓርትመንት  በየዓመቱ ለሚያዘጋጀው የሊደርሺፕ ፕሮግራም እንጂ ለሽልማት አይደለም ይላሉ፡፡  የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው የፓርቲውን ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃልን በጉዳዩና ኤርፖርት ላይ በገጠማቸው ችግር ዙርያ አነጋግራቸዋለች፡፡

ወደ አሜሪካ ለመጓዝ ኤርፖርት ከገቡ በኋላ ችግር እንደገጠመዎት ሰምቻለሁ፡፡ ችግሩ ምን ነበር?
በአሜሪካ መንግስት ተጋብዤ ለሶስት ሳምንት የምቆይበት “ወጣት የአፍሪካ መሪዎች” የሚል ፕሮግራም ነበር፡፡ በሉፍታንዛ ነበረ የምሄደው። በኤርፖርት ውስጥ አስፈላጊውን ሂደት ሁሉ አልፌ የኢሚግሬሽንና ደህንነት ሰዎች ፎቶ ወስደው ፓስፖርቴን ተቀበሉኝና አንደኛው አለቆቹ ጋር ይዞኝ ሄደ፡፡ ለሶስት ሰዓት ያህል አንድ ክፍል ውስጥ አቆዩኝ፡፡ መጨረሻ ላይ ከፓስፖርቴ ውስጥ አንድ ገፅ ነቅለው አውጥተው … “አንድ ገፅ ወጥታለች” ብሎ ቀዶ አመጣልኝ … እቃዬ አውሮፕላኑ ውስጥ ገብቶ ነበር፤ እሱንም አወረዱት፡፡ ባለፈው ሰኞ ነበር አሜሪካ መገኘት የነበረብኝ፤ ለጊዜው ተስተጓጉሏል።
የአሜሪካ መንግስት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል እንደሸለማችሁ ባለፈው ሳምንት በፓርቲያችሁ ልሳን ላይ ተዘግቧል፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ዕድሜው አጭር ከመሆኑ አንፃር ሽልማቱ ይገባናል ትላላችሁ?
ኢትዮጵያ ከዓለም የመጨረሻ ድሃ አገር ናት፡፡ አገሪቱን ከድህነት ለማውጣት የልጆቻችንን ዕድሜ የሚጠይቅ ተከታታይ ሥራ እና ትግል የሚያስፈልገው ነው፡፡ ሥራችንን የምትለኪው ግን በአንፃራዊነት ነው፡፡ ለምሳሌ ሰልፍ የሚባል ነገር ለስምንት አመት ኢትዮጵያ ውስጥ የማይታሰብ ነበር፡፡ አሁን ግን ሁሉም ፓርቲዎች ሰልፍና የአደባባይ የፖለቲካ ስራን እንደ ባህል እየያዙትና፤ እየተነቃቁም ናቸው። የሌሎች ፓርቲ አመራሮች “ህዝቡ ፈርቷል፤ ሰልፍ አይወጣም፣ አይተባበረንም” በሚል ዝም ብለው የመግለጫ ስራ ነበር የሚሰሩት፡፡ አሁን  ነገሮች ተለውጠዋል፡፡ አዲሱ ትውልድ በፊት ተከታይ እንጂ የራሱ ሀሳብ ኖሮት የሚሳተፍ አልነበረም። በሰማያዊ ፓርቲ ውስጥ ግን ሌት ተቀን የሚተጉ ሰዎችን ታያለሽ… እስከመታሰርም ደርሰዋል፡፡ ይህም የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡ የሚታየው የተፈጠረው የፖለቲካ መነቃቃትና ግንዛቤ ነው እንጂ የሀገራችንን ችግር ሰማያዊ ፓርቲ ፈትቶ ይጨርሰዋል ወይ ብትይ …. ትውልዱም የሚጨርሰው አይመስለኝም። ብዙ ተከታታይ ስራዎች ይጠይቃል፡፡ ከነበርንበት ጨለማ አንፃር ነው መታየት ያለበት፡፡ ቅንጅት በመፍረሱ ህዝቡ  ተስፋ ቆርጧል፡፡ ኢህአዴግ ጠቅላይ  በመሆኑና አፋኝ አዋጅ በመያዙ ዘላለማዊ ይመስል ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ያንን አስቸጋሪ ሁኔታ ወደ ይቻላል በማምጣትና መነቃቃት በመፍጠር የፖለቲካ ድባቡን ቀይሮታል፡፡ ይሄ ደግሞ ረጅም ጊዜንና ትልቅ ስራን የሚጠይቅ ነበር፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ግን በአጭር ጊዜ ይሄንን ማድረግ ችሏል፡፡ ከዚህ መንፈስ ነው የሚታየው እንጂ እኛ ብዙ ሰራን ብለን አንኩራራም፡፡ ገና ብዙ ስራ ነው የሚቀረን፤ ወደፊትም ብዙ እንሰራለን፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ አሁን በዘረዘሩልኝ ምክንያቶች በአሜሪካ መንግስት “የአፍሪካ ስኬታማ ወጣት መሪ” በሚል ሸልሞታል፤ ሽልማቱም ይገባናል እያሉኝ ነው?
አዎ .. በደንብ ተሸልመናል፡፡ ሽልማቱም ይገባናል፡፡ ሽልማቱ ይገባናል ስንል ግን አሜሪካኖች አይደሉም የሚሸልሙንና የሚያወድሱን፡፡ ግን በራሳቸው መመዘኛ እኛን መምረጣቸው መልካም ነገር ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ የሚያድግ ፓርቲ ነው፡፡ በኢትዮጵያ 70 ከመቶ የሚሆነው ህዝብ ወጣት ነው፡፡ ወጣቱን ሊወክል የሚችል ፓርቲ ነው፡፡ አዲስ አስተሳሰብን እንደፈጠረ ሃይል፣ ሽልማትን አስበን አይደለም የምንሰራው፡፡ ከዚህ በላይ ለሃገራችን ብዙ መስራት ይጠበቅብናል፡፡
በየጊዜው የተለያዩ ፖለቲከኞች ለህዝብ የገቡትን ቃል ሳይፈጽሙ ሸርተት ይላሉ፡፡ ህዝቡን ከዚህ ዓይነቱ ጥርጣሬ እንዴት ማውጣት ይቻላል ይላሉ?
ህልም ተፈርቶ ሳይተኛ አይታደርም፡፡ ከዚህ በፊት ኢትዮጵያ ውስጥ በተደጋጋሚ ውጤት ያልመጣው የግለሰብ ፖለቲካ በመሆኑና ፖለቲካው በሰዎቹ ስብዕና ላይ በመመስረቱ ነበር፡፡ ይሄም ትግሉን ጎድቷል፡፡ ለዚህ መፍትሔው ትግሉን ህዝባዊ ማድረግና በአንድ ሰው ላይ አለመንጠልጠል ነው፡፡ ህዝቡ ፖለቲካውን የራሴ ነው ብሎ መያዝ አለበት፡፡ ግለሰቦች ሲሄዱ ሌሎች ይተካሉ፡፡
ኢትዮጵያ የወላድ መካን አይደለችም፤ ብዙ ልጆች አሏት፡፡ ፖለቲካውን የጋራ ካደረግነው የህዝቡ ስጋት ይቀንሳል፡፡ ፖለቲካ የዜግነት ጉዳይ ነው፤ ሁሉም መሳተፍ አለበት፡፡ ያ በሆነ ጊዜ ራሳቸውን ብቻ ለአገር ጠቃሚ አድርገው የሚያስቡ ሰዎች መመፃደቃቸውን ያቆማሉ፡፡ ያኔ መግነንም አምባገነንነትም ይጠፋል፡፡ ፓርቲውም ህዝባዊነት ይኖረዋል ማለት ነው፡፡ የሰማያዊ ፓርቲ ልጆች የትኛውም ቦታ ላይ ተወዳድረውና ሰርተው መኖር የሚችሉ ናቸው፡፡ በዚህ በአሰልቺና በተጠላ ፖለቲካ ውስጥ የገቡት የአገር ፍቅር ስላላቸው ነው፡፡ የአገር ፍቅር ደግሞ ከየትኛውም ሽልማትና ሞገስ በላይ ነው፡፡   
ከወር በፊት ለፓርቲ ሥራ ወደ አሜሪካና አውሮፓ ተጉዘው ነበር፡፡ የተለያዩ ስብሰባዎችንም ከዳያስፖራው ጋር አድርጋችኋል፡፡ በዚህ ጉዞ ዋና ዓላማችሁ ምን ነበር?
ሁለት ወር ነው የቆየሁት፤ አውሮፓ አስራ አምስት ቀን፣ አሜሪካ 45 ቀን ያህል፡፡ አትላንታ፣ ሳንሆዜ፣ ቦስተን፣ ላስቬጋስ፣ ሎስአንጀለስ፣ ሲያትል… ነበርኩ። የመጀመሪያ ስብሰባዬ ዲሲ ነበር፡፡ የስብሰባው ዓላማ ሰማያዊ ፓርቲ የተመሰረተባቸውን መሰረታዊ አላማዎችና ምሰሶዎችን ማስተዋወቅ ነበር፡፡ እዚህም አብዛኛውን ቅዳሜና እሁድ ምሁራንን ቢሮዋችን ውስጥ እየጋበዝን በፀረ ሽብር ህጉ፣ በመሬት ፖሊሲ፣ በአጠቃላይ በኢኮኖሚ በታሪካችን ዙሪያ በመወያየት ሰማያዊ ፓርቲ ያለውን አቋም ለህዝብ በተደጋጋሚ ይገልጽ፣ ያስተምር ነበር፡፡ የአሜሪካና አውሮፓ ጉዞ ዓላማ፣ በውጭ ያለው ኢትዮጵያዊ ለሰማያዊ ፓርቲ ሀሳቦችና ፕሮግራሞች ድጋፍ እንዲሰጥና የትግል ስልቶቻችንንም ጭምር ለማስተዋወቅ ነበር፡፡
ሰማያዊ ፓርቲ የቅስቀሳ ሀይል እንጂ ድርጅታዊ መዋቅር የለውም፤ የንቅናቄ ፓርቲ ነው፤ የበሰለ ፖለቲካ አያራምድም የሚል ትችት ይሰነዘርባችኋል? እርስዎ ምን ይላሉ?
የሞተን ፖለቲካ ልታነሺ የምትችይው፤ ህዝብ ሲከተልሽና መነቃቃትን መፍጠር የምትችይው የአገሪቱን ችግር በሚገባ መረዳት ሲቻል፣ ለዚያ ችግር መፍትሄ ሊሆን የሚችል ቀጥተኛ ፖሊሲ ሲኖር፣ ፖሊሲውን ለማስፈፀም ደግሞ ብቃት ያለው አመራር ሲኖር ነው ህዝቡ የሚነቃነቀው፡፡ በስልጣን ላይ የተቀመጡ ሰዎች ፖሊሲ አላቸው፤ ሰማያዊ ፓርቲዎች ግን ፖሊሲ የላቸውም ቢባል ለአመለካከት የማይመች ነው የሚሆነው፡፡ በመሰረቱ አንድ ሰው ሊነቃነቅ የሚችለው  የሚያምንበት ነገር ሲኖር ነው። መነቃነቅ ከተፈጠረ እምነት አለ፡፡
ተቃዋሚ ፓርቲዎች በህብረት ለመስራት የትብብርና የውህደት እንቅስቃሴ ላይ ቢሆኑም ሰማያዊ ፓርቲ ለውህደት ዳተኝነት ይታይበታል የሚል ትችት ይሰነዘርበታል…
በኢትዮጵያ የ40 ዓመት የፖለቲካ ፓርቲዎች ታሪክ “ዛሬ ተዋህደው፤ ነገ ፈረሱ” ሲባል ነው የምናውቀው፡፡ ይሄ እንዲቀጥል አንፈልግም፡፡ ስለዚህም የውህደትንና የጥምረትን ነገር በጥንቃቄ መመርመር እንፈልጋለን፡፡ በሆይሆይታ የሚፈጠሩ ጥምረቶችና ውህደቶች ውጤቱ ሲያመጡ አልታየም። ለምሳሌ አንድነት ወደ መድረክ የገባው በጣም ፈጥኖ ስለነበር ራሱን ጎድቷል፡፡ እናም አንድነት ከመድረክ ታገደ ተባለ፡፡ ሰላሳ ሶስት ፓርቲዎች ተቋቁመው ምንም ነገር ሳይፈይዱ ነው የከሰሙት። በቅርቡ ደግሞ “አንድነትና መኢአድ ለውህደት እየተነጋገሩ ነው” ሲባል ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ተቋረጠ ተብሏል፡፡ እኛ ጥናት ሳይደረግ በፍጥነት ሮጠን ወደ ውህደት አንገባም፡፡ ወደ ፖለቲካው ያልገባ አዲሱ ትውልድ አለ፤ ፓርቲዎች አካባቢ ጊዜ ከምናጠፋ እዛ ላይ አተኩረን ህዝብ ውስጥ ብንሰራ ጉልበትም፣ ሀይልም፣ ዕውቀትም ገንዘብም አለ የሚል አቋም ይዘን ነው የምንንቀሳቀሰው፡፡ በመርህ ደረጃ ግን ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር ለመስራት ሰማያዊ ፓርቲ ዝግጁ ነው፡፡
የምርጫ ስነ ምግባር ኮዱን አንፈርምም ብላችኋል፡፡ ለምንድነው ለመፈረም ያልፈለጋችሁት?
አንድ ህግ በሀገር ደረጃ ህግ ሆኖ ከወጣ በኋላ መፈረም አለመፈረም አስገዳጅ አይደለም፤ ትክክለኛም አሰራር አይደለም፡፡ ለምሳሌ የማናምንባቸው አዋጆች ሁሉ ወጥተዋል፡፡ የፀረ-ሽብር አዋጅ፣ የመሬት ሊዝ አዋጅ፣ የሲቪክ ማህበራት ማደራጃ፣ የሚዲያና የመረጃ ነፃነት አዋጅ ወጥተዋል፡፡ እነዚህን አዋጆች ሰማያዊ ፓርቲ አፋኝ አዋጆች ናቸው ብሎ ያምናል፡፡ ህግ ሆነው ከወጡ በኋላ ግን ህገመንግስታዊ በሆነ መንገድ እስከ ምንቀይራቸው ድረስ ለአዋጆቹ መገዛት ግዴታችን ነው፡፡ የስነ ምግባር ደንብና አዋጅ በፓርላማ ህግ ሆኖ ፀድቋል፤ ለእሱ ብቻ መፈረም አያስፈልግም። አዋጅ በወጣ ቁጥር እኮ አንፈርምም፡፡ አጀንዳ ሆኖም መቅረብ የለበትም፡፡ ኢህአዴግ ለድርድር እንቅፋት ለመፍጠር ሲፈልግ ያመጣው ነው፡፡

  • በውዝግብ ታጅቦ የገሰገሰው ታላቁ የህዳሴ ግድብ በሦስተኛ ዓመቱ ዋዜማ
  • የግብፅ ግድቡን የማሰናከል ዓለም አቀፍ ጥረት ቀጥሏል

         የአባይ ውሀ ከሰማኒያ አምስት በመቶ በላይ ከኢትዮጵያ የሚመነጭ ቢሆንም፤ አባይ የግብፅ የብቻዋ ሲሳይ እንደሆነ ሲታሰብና ሲነገር  ኖሯል። ከፖለቲከኞች ዲስኩር በተጨማሪ፣ የግብፅ አፈ-ታሪኮችም አባይን “የብቻችን ፀጋ ነው” እያሉ ለህፃን ለአዋቂው እየተረኩና ከትውልድ ትውልድ እየተሻገሩ ለዘመናት ዘልቀዋል፡፡ “ያለ ግብጽ ፈቃድ አባይን የሚነካ አይኖርም” በሚል ከዘመኑ ቅኝ ገዢ ከእንግሊዝ ጋር የተፈራረሙትን ውልም፤ የአገሪቱ ውድ ሰነድ እንደሆነ ተደርጐ ሲቆጠር ምዕተዓመት ተቆጠረ፡፡  
በ1956 የግብፁ ፕሬዚዳንት ጋማል አብዱል ናስር፣ የአስዋንን ግድብ መገንባት እንደጀመሩ ለአገራቸው አበሰሩ፡፡ ግንባታው ከተጠናቀቀ በኋላ፤ ይሄውና  ግብፃውያን እስከዛሬ በየአመቱ ከሚያከብሯቸው ታላላቅ ህዝባዊ በዓላት መካከል አንዱ ሆነ፡፡ ከወንዙ ጉዳትን እንጂ ቅንጣት ጥቅም ሳታገኝ የኖረችው ኢትዮጵያ፤ ውሃውን ስራ ላይ የማዋል ወይም ትልቅ ግድብ የመገንባት አቅም አልነበራትም፡፡ ግን ሽንፈትን ተቀብላ አልተቀመጠችም፡፡ በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈረሙት የአባይ ውሎች ላይ ተቃውሞዋን በተደጋጋሚ ገልፃለች፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአፄ ሃይለሥላሴ ዘመን መንግስት በአባይ ላይ ትልቁን ግድብ ሳይቀር ለመገንባት የሚረዱ ጥናቶች እንዲካሄዱ ተደርጓል። የኢትዮጵያ ተቃዋሞና እንቅስቃሴ ቀስ በቀስ እየጠነከረና ብልህነትን እየተላበሰ የመጣው ደግሞ ባለፉት 20 አመታት ነው፡፡ ሁሉንም የወንዙ ተጋሪ አገሮች ያላካተተ የቅኝ ግዛት ውል ተቀባይነት እንደሌለው በመግለጽ፣ ሁሉን አቀፍ በሆነ መልኩ አዲስ ውል እንዲተካ መጣጣር ጀመረች፡፡ በዚህም የአብዛኞቹን የተፋሰሱ አገራት ይሁንታ ያገኘ “የኢንቴቤ ስምምነት” የተሰኘ አዲስ ውል ተፈረመ። በዚህ መሃል ነው፤ እንደ መሞከሪያ የበለስ ሃይል ማመንጫ ግድብ በጣና ሃይቅ ግድም የተገነባው።  በጥቂቱም ቢሆን ለመስኖ የሚያገለግለው የበለስ ግድብ፤  ከንትርክ ባያመልጥም በአለማቀፍ ደረጃ ትልቅ የውዝግብ ርዕሰ ጉዳይ ከመሆን አምልጧል። እንዲያም ሆኖ፣ የግብጽና የኢትዮጵያ ክርክር አልተቋረጠም፡፡ እንዲያውም እየባሰበት መጥቷል፡፡
ግብፃውያን የቅኝ ግዛት ውሎችን ይዘው ይከራከራሉ፡፡ ኢትዮጵያ ደግሞ በኢንቴቤ ስምምነት መሰረት ፍትሀዊ የውሀ ክፍፍል ይኑር ትላለች፡፡ የሁለቱ አገራት የዘመናት ክርክር ወደ ተጋጋለ አዲስ ውዝግብ የተሸጋገረው በ2003 ዓ.ም ነው፡፡   
ኢትዮጵያ ለኤሌክትሪክ ሀይል ማመንጫ ጥቅም የሚውል የታላቁ የህዳሴ ግድብን በአባይ ወንዝ ላይ እገነባለሁ  ስትል አስታወቀች፡፡  የግብፅና የሱዳን ጥቅም ላይ ይህ ነው የሚባል ለውጥ አያመጣም ተብሎ የተጀመረው  የግድብ ግንባታ፣ ሰኞ ሶስተኛ አመቱን ያከብራል፡፡ ባለፉት ሶስት አመታት ግብፅ ግድቡን አስመልክቶ የምትይዛቸው አቋሞች፣ የምትሰጣቸው መግለጫዎች እና የምታንኳኳቸው በሮች ድብልቅልቅ ያሉና እርስ በርስ የሚጣረሱ ቢሆኑም፣ ግብፅ አሁንም ግድቡ እውን እንዳይሆን መጎትጎቷን ቀጥላለች፡፡ ከኢትዮጵያ አቋሞች ጋር ባለፉት ሦስት ዓመታት ጐልተው የወጡ የግብፅ አቋሞችንና እርምጃዎችን እንቃኝ፡፡
ታሪካዊ መብት እና የቅኝ ግዛት ውሎች
የታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ በኢትዮጵያ በኩል ይፋ ከተደረገ በኋላ ጐልተው የወጡ ብዙዎቹ የግብጽ መከራከሪያዎች፤ ከዚያም በፊት ሲሰነዘሩ የነበሩ ናቸው፡፡ አባይ ሲነሳ የሚቀርበው መከራከሪያ በቅኝ ግዛት ዘመን የተፈረሙ ውሎች ናቸው - የተፋሰሱን አገራት ያላካተቱት  ውሎች ቢሆኑም፡፡ “ግብፅ በአባይ ላይ ታሪካዊና ሕጋዊ መብት አላት፡፡ ኢትዮጵያ  በህዳሴ ግድብ ግንባታ የግብጽን መብት ጥሳለች፡፡ ለግብፅ እና ለሱዳን የውሀ ክፍፍል የሚሰጡ የቅኝ ግዛት ውሎችንም ኢትዮጵያ አፍርሳለች” በማለት ግብፆች የግድብ ግንባታውን ለማስቆም ይጥራሉ፡፡  አብዛኛውን ጊዜ የሚጠቀሱት የቅኝ ግዛት ውሎች ሁለት ናቸው፡፡  በ1929 እንግሊዝና ግብጽ የተፈራረሙት ውል አንዱ ነው፡፡ ሌላኛው ደግሞ ግብጽ እና ሱዳን በ1959 የተፈራረሙት ውል፡፡  ሰሞኑን ደግሞ “ኢትዮጵያም የቅኝ ግዛት ውሎች አካል ነበረች” ለማለት በሚመስል መንገድ፤ “አፄ ምኒልክ በ1902 ከእንግሊዝ ጋር የተፈራረሙት ውል ተጥሷል” በሚል ኢትዮጵያ ወንዙን ያለግብፅ ፈቃድ ምንም ማድረግ እንደማትችል አስረግጠው እየተናገሩ ይገኛሉ፡፡ ይህን ሀሳብ የሚያራምዱት ወገኖች፣ የግድቡ ግንባታ ግብፅ ላይ ጦርነት ከማወጅ የሚተናነስ አይደለም በማለት  ኢትዮጵያ ግንባታውን እንድታቆም ይሞግታሉ፡፡ መሞገት ብቻ አይደለም፤ የግብፅ ባለስልጣኖች በይፋ የሚነገሩ ድርድሮች እና ጉብኝቶችን ከማድረግ በተጨማሪ ይፋ ያልተደረጉ እንቅስቃሴዎችን እያካሄዱ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ጉዳትን መቀነስ
የሕዳሴን ግድብ ግንባታ ለማስቆም ግብጽ የምታካሂደው ዘመቻ ቀላል ባይሆንም፤ ዘመቻው ይሳካል የሚል እምነት የሌላቸው ቡድኖች በበኩላቸው፤ የራሳቸውን አማራጭ ዘዴ አቅርበዋል። በተለይ “የአባይ ተፋሰስ ቡድን” በሚል የተቋቋመው የግብፃዊያን ቡድን፤ በዩኒቨርስቲ የኢንጂነሪንግ እና የግብርና ፕሮፌሰሮችን፣ የቀድሞ የውሀ እና የመስኖ ሚኒስትሮችን  እንዲሁም ኢትዮጵያ፣ ሱዳን እና ግብፅ ባቋቋሙት የኤክስፐርቶች ቡድን ውስጥ የግብፅ ተወካይ የነበሩ ባለሙያዎችን ያካትታል። ግብፅ የግድቡን ግንባታ የምታስቆምበት ደረጃ ላይ አይደለችም የሚለው ይሄው ቡድን፤ አሁን የሚያዋጣን ድርድሩን የግብፅን ጉዳት በሚቀንስ መንገድ ማስኬድ ነው ይላል፡፡ “ከግብፅ ጥቅም አኳያ ትክክለኛው የድርድር አካሄድ የግድቡን ግንባታ ማስቆም መሆን ነበረበት፤ ነገር ግን ይህ አማራጭ አሁን የለም፡፡ ዘግይቷል፤ ጊዜው አልፏል” የሚሉት የቡድኑ አባላት፤ኢትዮጵያ የግድቡን ግንባታ ከፅንሰ ሀሳብ ወደ ተግባር ለውጣዋለች በማለት ያስረዳሉ፡፡ ስለዚህ አሁን ባለው ሁኔታ የግብፅ ዓላማና እንቅስቃሴ በግድቡ ምክንያት ሊደርስባት የሚችለውን ጉዳት ለመቀነስ ያነጣጠረ መሆን እንዳለበት የሚገልፁት የቡድኑ አባላት፤ ለግብፅ የውሀ ፍላጎት ስጋት የሚሆነው የግድቡ መጠን ስለሆነ የግብፅ መንግስት ኢትዮጵያ የግድቡን መጠን እንድትቀንስ ማግባባት፣ ካልሆነም ጫና ማሳደር እንዳለበት ያሳስባሉ፡፡
የግብፅ የውሀና የመስኖ ሚኒስትር መሀመድ አብዱል ሙጣሊብም፣ ግብፅ ከታሪካዊ መብቷ እና በቅኝ ግዛት ዘመን ከተሰጣት የውሀ  ኮታ አንዲት ጠብታ አሳልፋ አትሰጥም በማለት በየካቲት ወር በሰጡት አስተያየት፤ የኢትዮጵያን የልማት ፕሮጀክቶች ብንደግፍም ከኢትዮጵያ ጋር መደራደር በቃን ብለው ነበር፡፡ ቱርክ ለግድቡ ግንባታ ባለሙያዎችን ለመላክ ተስማምታለች በማለት ተቃውሞአቸውን የገለፁት እኚሁ ሚኒስትር፤ ቱርክ አለማቀፍ ህጐችን በመጣስና የጐረቤት አገራትን ተቃውሞ ቸል በማለት አታቱርክ የተባለ ግድብ ገንባታ፤ የሶሪያና የኢራቅ ህዝቦችን ለውሀ ጥም ዳርጋለች ብለዋል፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ቱርክ አይደለችም በማለት የሕዳሴ ግድብ ግንባታን ሚኒስትሩ ካጣጣሉ በኋላ፤ ግብፅም ሶሪያ ወይም ኢራቅ አይደለችም በማለት ፎክረዋል፡፡ እንደገና በዚያው ወር  ደግሞ  ኢትዮጵያ  ትልቁን ግድብ በማቆም ሁለት ትንንሽ ግድቦችን በመስራት የኤሌክትሪክ ሀይል ማመንጨት ትችላለች ብለዋል፡፡  
የግብፅ የቀድሞ የውሀ እና የመስኖ ሚኒስትር ግን ያን ያህልም ውጤት አይታያቸውም፡፡ የአባይ ተፋሰስ ቡድን አባል የሆኑት እኚሁ የቀድሞ ሚኒስትር፤ የግብፅን ጉዳት መቀነስ በሚለው ሀሳብ ቢስማሙም፤ በቅርቡ በሰጡት አስተያየት የግብፅን መንግስት “ነፈዝ” ሲሉ አጣጥለዋል፡፡ “በህዳሴው ግድብ ዙሪያ ግብፅ እየተቀደመች ነው፡፡ ውሳኔዋ በእጅጉ የዘገየና  ውጤት የሌለው ነው” በማለት መንግስትን ሲተቹ፤ “የተፋሰሱን አገሮች አስመልክቶ ግብፅ ያላት መረጃ ያልተሟላና ደረጃውን ያልጠበቀ ነው፡፡ በዚህ መስክ የብቁ ባለሙያ እጥረት ገጥሟታል” ብለዋል። እንዲያም ሆኖ፤ የግድብ ግንባታውን ለማስቆም አልያም ለማስተጓጐል በግብጽ የሚካሄደው ዘመቻ እየጠበበ ሳይሆን እየሰፋ፤ እየሰከነ ሳይሆን በየአቅጣጫው እየተወሳሰበ ሄዷል፡፡ ከውስብስብ ዘመቻዎቹ መካከል አንዱ፣ አለማቀፍ ትኩረት ላይ ያነጣጠረው አቅጣጫ ይጠቀሳል፡፡  
ኢትዮጵያን በዓለማቀፍ ተቋማት መሞገት እና የፋይናንስ ድጋፍ  ማሳጣት
የግድቡን ጉዳይ አለምአቀፋዊ ገፅታ የማላበስ አቅጣጫ በመያዝ፣ ግብፃውያኑ በሚያካሂዱት ዘመቻ ኢትዮጵያ ግድቡን ለመገንባት እንዳትችል የገንዘብ ምንጮቿን ለማድረቅ፣ የቴክኒክ ድጋፍ የሚያሰጡ ወገኖችን ለማሳጣት አለምን እያዳረሱ ነው፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የፀጥታው ምክር ቤት የግድቡን ጉዳይ በአጀንዳ እንዲይዘው ለመገፋፋት ከተጀመረው አዲስ ጥረት በተጨማሪ፤ እንደወትሮው አለም አቀፍ የገንዘብ ተቋሞች ለኢትዮጵያ ገንዘብ እንዳይሰጡ ጫና የማሳደር ዘመቻም አልተቋረጠም፡፡ ሌላው የዚህ ዘመቻ አቅጣጫ፣ በአውሮፓና በአረብ አገራት ላይ በተለይም በሳኡዲ አረቢያ ላይ ያነጣጥራል፡፡
በግብፅ የአለም አቀፍ ትብብር ሚኒስቴር መስሪያ ቤት የአውሮፓ ክፍል ዋና ፀሀፊ የሆኑት አምባሳደር ጋማል ባዩሚ፤ “የግብጽ ጥረት ለህዳሴው ግድብ የቴክኒክ ድጋፍ የሚሰጡ አገሮች ፣ ኮንትራክተሮች እና ዝንባሌ ያላቸው የአውሮፓና የአረብ ወገኖች ላይ ማነጣጠር አለበት” በማለት ሰሞኑን በፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለመሳተፍ እንዲያስችላቸው በመከላከያው የነበራቸውን ኃላፊነት የለቀቁት የቀድሞው የግብፅ መከላከያ ሚኒስትርና ፕሬዚዳንት ፊልድ ማርሻል አብዱል ፈታህ አልሲሴ በራሺያ ያደረጉት ጉብኝት ተጠቃሽ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በየካቲት ወር ወደ ጣልያን የተጓዙት የግብፅ የውሀ እና የመስኖ ሚኒስትርም፤ የጉብኝታቸው አላማ እንደተሳካ ሲያስረዱ፤ ጣሊያን የግብፅን ስጋት ተረድታለች፤ ጥረታችን በሌሎች የአውሮፓ አገሮችም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡
በሌላ በኩል ግብፅ በህዳሴው ግድብ ዙሪያ ሳኡዲ አረቢያ እንድታደራድር መጠየቋን ተከትሎ፤ የአረብ የውሀ ምክር ቤት ሃላፊ መሀሙድ አቡ ዘይድ ኢትዮጵያ ላይ ጫና ማሳደር ውጤታማ ሊሆን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡  የሳኡዲ አረቢያ፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች እና የኩዌት መንግስታት  ኢትዮጵያ ውስጥ ትልልቅ ፕሮጀክቶች እንዳሏቸው የተናገሩት አቡ ዘይድ፤ በእነዚህ መንግስታት በኩል ኢትዮጵያ ላይ ጫና ለማሳረፍ መሞከር ትልቅ ውጤት እንደሚያመጣ አምናለሁ ብለዋል፡፡ የአል አህራም የፖለቲካ ጥናቶች ማእከል የአፍሪካ ጉዳዮች ስፔሻሊስት ሀኒ ራስላን በበኩላቸው፤ በሳኡዲ አረቢያና በአሜሪካን መካከል ባለው የዲፕሎማሲ ግንኙነት በኩልም ኢትዮጵያ ላይ ጫና ለማሳደር ጥረት መደረግ አለበት ይላሉ፡፡
ዲሞክራቲክ ፒፕል ፓርቲ ፣ ኢጂፕሺያን አረብ ሶሻሊስት ፓርቲ እና  ጀስቲስ ፓርቲ የተባሉ የግብፅ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ደግሞ፣ የግድቡ ግንባታ እንዲቋረጥ ዘ ሄግ ለሚገኘው አለም አቀፍ  ፍርድ ቤት አቤቱታ አቅርበዋል፡፡ ነገር ግን ፍርድ ቤቱ በፓርቲዎች የሚቀርቡ አቤቱታዎችን የማየት ስልጣን የለውም፡፡
የፀጥታ እና የደህንነት ስጋት መፍጠር
የግድቡን ግንባታ የፀጥታና የደህንነት ስጋት ውስጥ መክተት፤ለዚህ ደግሞ የኢትዮጵያ መንግስት ተቃዋሚዎችን ከግብፅ ጎን ማሰለፍ የሚለው የሚገመት ግን ይፋ ይደረጋል ተብሎ ያልተጠበቀው አቅጣጫ ደግሞ መሀመድ ሞርሲ በስልጣን በነበሩበት ወቅት በታላቁ የህዳሴ ግድብ ዙሪያ ለመነጋገር የተጠራ የፖለቲካ ፓርቲዎች ስብስብ፣ ኢትዮጵያ የግድቡን ግንባታ የማታቋርጥ ከሆነ አገሪቱ በተለያዩ ወገኖች የተከፋፈለች መሆኗን እንደ ጥሩ አጋጣሚ በመውሰድ፣ እነዚህን ሀይሎች ከግብፅ ጎን ማሰለፍን እንደ አንድ አማራጭ እንደሚያዩ በቴሌቪዝን የቀጥታ ስርጭት ተላልፏል፡፡ ግድቡን ማጥቃት የሚለው በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት መተላለፉን አስመልክቶ የተለያዩ አስተያየቶች መሰጠታቸው የሚታወስ ሲሆን  ይህም ኢትዮጵያ ከግብፅ ጋር ለመገንባት እየሞከረች የነበረውን የመተማመን መንፈስ የሸረሸረ እንደሆነ ብዙዎች ይስማሙበታል፡፡  መሀመድ ሞርሲ፤ በዓመጽ እና በመፈንቅለ መንግስት ከስልጣን ከተወገዱ በኋላ የግብፅ የመከላከያ ሚኒስትር ለዋሽንግተን ፖስት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፤  ሞርሲ ኢትዮጵያን አስመልክቶ ከመከላከያ ሃይል ይሰጠው የነበረውን መረጃ በደንብ አይከታተልም ነበር፣ የግድቡን አደገኛነትና አጣዳፊነት አልገባውም፤ ግብፅ በናይል ላይ ያላት ቁጥጥር የብሄራዊ ስትራቴጂካዊ ጥቅም ጉዳይ ነው፤ ከመብቷ በተቃራኒ የሚደረግ ማንኛውም እንቅስቃሴ ሊፈነዳ የሚችል ጥቃት ነው ብለዋል፡፡
ከተፋሰሱ አገሮች ጋር መተባበር እና አዲስ ናይል መፍጠር
የግብፅ ዋና ዋና መከራከሪያዎችና ዘመቻዎች መልካቸው ባይቀየርም፤ ባለፉት ሦስት አመታት አድማጭን ግራ የሚያጋቡ ዝብርቅርቅ ሃሳቦችና መግለጫዎች ተሰጥተዋል፡፡ ግድቡን በጋራ እንገንባ ከሚለው ግብዣ ጀምሮ፤ የግብፅ ባለሙያዎች ግድቡ አካባቢ ቢሮ ተሰጥቷቸው ሁኔታዎችን ይከታተሉ እስከሚለው ጥያቄ ድረስ በየጊዜው ዥንጉርጉር ሃሳቦች ተደምጠዋል፡፡
ሰሞነኛው ርዕሰ ጉዳይ ደግሞ ከተፋሰሱ አገራት ጋር መተባበር እና አዲስ ናይል እንፍጠር የሚል እቅድ ነው፡፡ ከውጭ ኢትዮጵያ ላይ ጫና ማሳደር ያልቻልነው ከተፋሰሱ አገሮች ጋር ጠንካራ ትብብር ባለመፍጠራችን ነው የሚሉ የግብጽ ባለሙያዎች፤ ጣታቸውን በሁስኒ ሙባረክ ላይ ይቀስራሉ፡፡ ሙባረክ በአረብ ሊግና በአረቡ አለም ተሰሚነት ለማግኘት ለመግኘን  ሲጨነቁ፣ የኢትዮጵያ መሪዎች በተፋሰሱ አገራት ዘንድ ይሁንታ ለማግኘት በርትተው በመስራት ውጤታማ ሆነዋል ይላሉ እነዚሁ ባለሙያዎች፡፡ ኢትዮጵያ የቅኝ ግዛት ዘመን ውሎች በኢንቴቤ ስምምነት ተሰርዘዋል ብላ ከአብዛኞቹ የተፋሰሱ አገራት ጋር ስትፈራረም፤ ሙባረክ ግን ስልጣናቸውን ለማን እንደሚያወርሱ እና ምርጫ እንዴት እንደሚያጭበረብሩ በማሰብ ተጠምደው ነበር የሚሉት ባለሙያዎች፤  አሁንም የተፋሰሱን አገሮች ይሁንታ ለማግኘት ግብፅ መታተር አለባት ሲሉ ይመክራሉ፡፡  
ከሰሞኑ ከወደ ግብፅ እየተሰማ ያለ አዲስ እቅድም ከተፋሰሱ አገራት ጋር አዲስ ናይል የመፍጠር ሀሳብ ነው፡፡ ነጩን ናይል ከኮንጎ ወንዝ ጋር በማገናኘት ከእስከዛሬው በላቀ ሁኔታ ግብፅ በአመት 110 ቢሊዮን ኪዩቢክ ሜትር ውሀ እንድታገኝ ማድረግ ይቻላል በሚል የቀረበው እቅድ፤ የግብፅን የውሀ ስጋት ይቀርፋል ተብሏል፡፡ አዲስ አባይ እንደመፍጠር ነው በተባለለት በዚሁ እቅድ ላይ ሰሞኑን ጥያቄ የቀረበላቸው የግብፅ የውሀ እና የመስኖ ሚኒስትር፤ ፕሮጀክቱን ከቴክኒክ አኳያ እያጤኑት እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡ እቅዱን ለማሳካት የበርካታ አገራትን ትብብር ማግኘትና በደቡብ ሱዳን ትልቅ ግድብ መገንባት ያስፈልጋል፡፡ ይህን  እውን ለማድረግ  የሚሰራው ግድብ ከኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ የበለጠ መሆኑን በመጥቀስ ትችት የሰነዘሩ ወገኖች፤ ኢትዮጵያ የህዳሴን ግድብ መጠን እንድትቀንስ እየጐተጐተች ያለችው ግብጽ፤ ከዚያ የበለጠ ግድብ ለመገንባት ጥናት እያካሄደች መሆኗ አስገራሚ ነው ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ
የህዳሴ ግድብ ግንባታ በየሳምንቱ ሰባቱንም ቀናት፣ በየእለቱም ሀያ አራት ሰአት እየተሰራ ሲሆን ሰላሳ ሁለት በመቶ ደርሷል፡፡ በተለያዩ መንገዶች ከግብፅ ለሚሰነዘሩ አስተያየቶች እና ለሚካሄዱ ዘመቻዎች ባለፉት ሶስት አመታት ከኢትዮጵያ የተሰጡ ምላሾች ተመሳሳይ ናቸው፡፡  ኢትዮጵያ የምትገነባው ግድብ ግብፅን እና ሱዳንን እንደማይጎዳ፣ የግድቡ መጠን እንደማይቀንስ፣ ግንባታው ለሰከንድ እንደማይቆም፣ የግንባታው ወጪም በኢትዮጵያውያን እንደሚሸፈን እና የቅኝ ግዛት ውል በኢንቴቤው ስምምነት እንደተተካ በመግለጽ ነው ኢትዮጵያ ስትከራከር የቆየችው፡፡


  • “በመንገድ ላይ ለሚደርሱ አደጋዎች የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ተጠያቂ ነው”
  • “መንግሥትን በሰራው ጥፋት መክሰስ ህገ-መንግስታዊ መብት ነው” - የህግ ባለሙያ

ለአዛውንቱ አቶ ተስፋዬ ኪዳኔ መስከረም 10 ቀን 2006 ዓ.ም መልካም ቀን አልነበረም፡፡ ከመ/ቤታቸው ወጥተው ወደ ቤታቸው እያመሩ ነበር፡፡ ከ5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ወደ ጌጃ ሰፈር በሚወስደው መንገድ ኮንዶሚኒየም ቤቶች አካባቢ ሲደርሱ በፍፁም ያልጠበቁት አስደንጋጭ አደጋ አጋጠማቸው፡፡ መንገድ ዳር ከሚገኝ ጉድጓድ ውስጥ ገብተው እግራቸው ተሰበረ፡፡
ከድንጋጤ ጋር ሙሉ ኃይላቸውን አሰባስበው ባሰሙት የድረሱልኝ ጥሪ፣ የአካባቢው ሰዎችና የእሳት አደጋ ሰራተኞች ተረባርበው ከጉድጓዱ በማውጣት ወደ ባልቻ ሆስፒታል ለህክምና ወሰዷቸው፡፡ በሆስፒታሉ ለ20 ቀን ተኝተው ከ23 ሺህ ብር በላይ አውጥተው ቢታከሙም እንደተመኙት በፍጥነት ከጉዳታቸው አገግመው በእግራቸው ቆመው ለመሄድ አልቻሉም። ይኸውና ላለፉት 7 ወራት ከሰውና ከክራንች ድጋፍ መላቀቅ አቅቷቸዋል፡፡
አሁንም በተመላላሽ ህክምናቸውን እየተከታተሉ ሲሆን አቶ ተስፋዬ ለደረሰባቸው ጉዳት ኃላፊነት የሚወስድ አካል የትኛው እንደሆነ ባለማወቃቸው መብታቸውን ማስከበርና ካሳ ማግኘት እንዳልቻሉ ይናገራሉ። “መንገዱ ላይ የተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ ነው የገባሁት፣ ኃላፊነቱን መውሰድ የሚገባው የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ነው የሚል እምነት አለኝ። ነገር ግን አንድ ሰው የዚህ ዓይነት አደጋ ሲደርስበት በየትኛው የህግ አግባብ፣ ማንን መክሰስና መጠየቅ እንዳለበት አላውቅም” ብለዋል፡፡
እንደ አቶ ተስፋዬ ሁሉ ባለፉት 6 ወራት መንገድ ዳር ተቆፍረው ባልተከደኑ ጉድጓዶችና በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉ ኩሬዎች ውስጥ ገብተው 41 ሰዎች መሞታቸውን፣106 ሰዎች መቁሰላቸውን ከአዲስ አበባ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከልና መቆጣጠሪያ ኤጀንሲ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ ዓምና በግማሽ አመት ውስጥ 28 ሰዎች በተመሳሳይ አደጋ ሲሞቱ፣ 88 ሰዎች ቆስለዋል፡፡ ይህም ዘንድሮ የአደጋው መጠመን መጨመሩን ያመለክታል፡፡  
“በአዲስ አበባ መንገዶች ላይ በየአምስት ሜትሩ ጉድጓድ አለ፡፡ አብዛኞቹ ጉድጓዶቹ በአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ለፍሳሽ (ድሬኔጅ) መውረጃ የተቆፈሩ ናቸው፡፡ ለቴሌኮም፣ ለመብራት ኃይል ኬብሎችና ለመሰል አገልግሎት የሚቆፈሩም አሉ፡፡ ጉድጓዶቹ ትላልቅ ስለሆኑ ከሰው ቁመት በላይ እስከ 2 ሜትር ጥልቀት ያላቸው ናቸው” ይላሉ፤የአዲስ አበባ እሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከልና መቆጣጠር የኮሙኒኬሽ ኦፊሰር አቶ ንጋቱ ማሞ፡፡
ጉድጓዶቹ፣ በተለያዩ ምክንያቶች ክፍት ሊሆኑ ይችላሉ ያሉት አቶ ንጋቱ፤ ሕገ-ወጦች ክዳኑ  ላይ ያለውን ፌሮና ሌሎች ነገሮች ወስደው ክፍት ይተዋቸዋል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የጉድጓዶቹ ባለቤት የሆኑ ድርጅት ሠራተኞች ለሥራ ይከፍቱትና ሳይዘጉ ይተዋቸዋል፡፡ ሁሉም ጉድጓዶች ያሉት መንገድ ላይ ነው፡፡ እነዚህ ጉድጓዶች ብዙውን ጊዜ ጉዳት የሚያደርሱት በክረምትና በጭለማ ነው፡፡ በክረምት ፍሳሹ ሞልቶ አስፋልቱን ስለሚያጥለቀልቀው ጉድጓድ መኖሩ አይታወቅም፡፡ በጭለማም አይታይም፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ለመንገድ ግንባታ ጉድጓዶች ይቆፈራሉ፡፡ ጧት ሥራ ስትሄድ ያልነበረ ጉድጓድ፣ ማታ ስትመለስ ተቆፍሮ ይጠብቅሃል፡፡ በሥራ መግቢያና መውጫ ሰዓት ጉድጓድ ስለመኖሩ የማያውቅ እንግዳና ሌላውም ሰው ትራንስፖርት ለመያዝ ሲጋፋ ጉድጓዶቹ ውስጥ ወድቆ ሊጎዳ ይችላል፡፡
ይኼ በከተማው መኸልም የሚታይ ነው፡፡ ከመዲናዋ ወጣ ብለው በሚገኙ የልማት ማስፋፊያ አካባቢዎችም ለኢንቨስትመንት በማለት ንፋስ ስልክ ላፍቶ ወረዳ አንድና ሁለት፣ ቦሌ ቡልቡላ ወረዳ አንድ፣ ቦሌ ኤርፖርቶች ድርጅት ጀርባ፣ ኮልፌ ቀራንዮ ሚኪሌይላንድ አካባቢ፣ ሐና ማርያም፣ ገርጂ ጊዮርጊስ … አካባቢዎች ድንጋይና ማዕድን ለማውጣት ፈቃድ ወስደው የሚቆፍሩ አሉ። የሚፈልጉትን ነገር ካገኙ በኋላ ለቀው ሲሄዱ የቆፈሩትን ጉድጓድ ሳይከድኑት ክፍቱን ትተው ነው የሚሄዱት፡፡ ያ ቦታ ውሃ ይቋጥርና ኩሬ ይፈጥራል። እዚያ ውስጥ ዋና የማይችሉ ታዳጊዎችና ወጣቶች ገብተው ሲዋኙ ወይም ኮብልስቶን ጠራጊዎች የግል ንፅህና ለመጠበቅ ገብተው ሲታጠቡ ሰምጠው ይሞታሉ፡፡
ሰሞኑን እንኳ ሐና ማርያም አካባቢ ባለ ኩሬ ውስጥ አንድ የ10 ዓመት ታዳጊ ገብቶ ሬሳውን አውጥተናል፡፡ ኩሬው ብዙ ህይወት ነው የቀጠፈው። አቃቂ አካባቢ የውሃ ችግር ስላለ እዚያ አካባቢ ካለ ኩሬ ውሃ ለመቅዳት የሄደ የጋሪ ፈረስ  ከነጋሪው ኩሬው ውስጥ  ሰጥሞ ሞቶ አውጥተናል፡፡
ለእነዚህ አደጋዎች ተጠያቂዎቹ ድንጋይ ወይም ማዕድን ለማውጣት ቦታውን ቆፍረው ሲያበቁ ቦታውን ቀድሞ ወደነበረበት ሳይመልሱ ክፍቱን ትተው የሚሄዱ ድርጅቶችና አስፈጻሚ አካላት ናቸው፡፡ ቦታውን ለመቆፈር ከአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ፈቃድ ሲያወጡ፣ ሲበቃቸው መልሰው ለመክደን ግዴታ ይገባሉ፡፡ ባለስልጣን መ/ቤቱም “ቃላችሁን ባታከብሩ” ብሎ ጉድጓዱን መክደን የሚያስችል ከፍተኛ ገንዘብ በመያዣ ይቀበላል። ነገር ግን ድርጅቶቹ በቸልተኝነት ወይም በሌላ ምክንያት የቆፈሩትን ጉድጓድ ሳይዘጉ ቢሄዱ አይጠየቁም ወይም አስፈጻሚው አካል ተከታትሎ ለመያዣ በተቀበለው ገንዘብ ጉድጓዱ እንዲዘጋ አያደርግም፡፡ እኛ አገር ጥሩ ጥሩ ሕጎች አሉ፡፡ ነገር ግን ተከታትሎ የሚያስፈጽም አካል የለም፡፡
በዚህ የተነሳ ባለፉት 6 ወራት ውስጥ ብቻ 41 ሰዎች ባልተከደነ የመንገድ ጉድጓድና ኩሬ ውስጥ ገብተው ሕይወታቸውን አጥተዋል፡፡ ከ15 ቀን በፊት ሜክሲኮ ከፌዴራል ፖሊስ ዋና ጽ/ቤት ፊት ለፊት አንድ የ32 ዓመት ወጣት ለቀላል ባቡር መንገድ በተቆፈረ ጉድጓድ ውስጥ ገብቶ ሞቷል፡፡ ጊዜው ትንሽ ቆየት ብሏል እንጂ አንድ ሰው በቀድሞው የአፍሪካ ኅብረት ድርጅት፣ በአሁኑ የአፍሪካ አንድነት አካባቢ ባለ ጉድጓድ ውስጥ ገብቶ 5 ቀን ከቆየ በኋላ እንዳጋጣሚ ሆኖ ከእነሕይወቱ ሊወጣ ችሏል፡፡ ያ ሰው ዕድለኛ ነው ማለት ይቻላል፡፡ አንዲት ልጅ በአጋጣሚ ከጉድጓድ ውስጥ ድምፅ ትሰማለች። ለማረጋገጥ ጠጋ ስትል ሰው አየች፡፡ ልጅቷ እዚህ (እሳት አደጋ) የሚሰራ ወንድም ስለነበራት፣ ደውላ ስላየችው ነገር ነገረችው፡፡ በአጋጣሚ ወንድምየው ዕረፍት ላይ ስለነበር፣ ደውሎ ነገረንና ሄደን አወጣነው፡፡ ያ ሰው አሁንም በሕይወት አለ፡፡ የሀይገር ሹፌር ሲሆን ትዳር መስርቶ እየኖረ ነው። ይኼ አደጋው ሲደርስ ዘመድ ወይም በአካባቢው የነበሩት ሰዎች ደውለውልን ያወጣናቸው ናቸው። ለእኛ ሳይደወል ዘመድ ወይም የአካባቢው ሰዎች ከጉድጓድ አውጥተው ወደ ቤትና ወደ ሐኪም ቤት የወሰዷቸው ወይም የቀበሯቸው በርካታ ናቸው፤ ቤት ይቁጠራቸው፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ ከአዲስ አበባ መንገዶች ባለሥልጣን ጋር ብዙ ጊዜ ተወያይተናል፡፡ እኔ ራሴ ከባለሥልጣኑ ኃላፊ ከኢንጂነር ፍቃዱ ኃይሌ ጋር ተነጋግሬአለሁ፡፡ ምንም መፍትሔ ያልተገኘለት ችግር ሆኖ ቆይቷል፡፡ ለልማት ተብሎ ተቆፍሮ በሚፈጠር ኩሬ ውስጥ በሳምንት አንድ ወይም ሁለት ሰው ገብቶ ይሞታል፡፡ በዚህ የተነሳ በዜጎች ላይ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰ ነው፡፡ እኛ ማድረግ የምንችለው ጉድጓድ ወይም ኩሬ ውስጥ ገብተው የሞቱትን ሬሳ አውጥተን ለፖሊስ ማስረከብ፣ አምቡላንስ ስላለን ተጎድተው በህይወት ያሉትን ህክምና ወደሚያገኙበት ማድረስ ነው፡፡ ከዚህ በተረፈ ከኩሬ ውስጥ ሬሳ ስናወጣ በአካባቢው ላሉ ሰዎች ትምህርት እንሰጣለን፡፡ ነገር ግን እዋኛለሁ ብሎ ለሚሄድ ሰው ጠባቂ ማቆም አንችልም፡፡ ልማት ሲካሄድ ያለ ቁፋሮ ሊካሄድ አይችልም፡፡ ስለዚህ ጉድጓድ ሲፈጠር መከለል አለበት፡፡ በአካባቢው አደጋ መኖሩን የሚጠቁሙ ዓለም አቀፍ ምልክቶች ስላሉ፣ እነሱ ጉድጓዱ ጋ ከመድረሱ ከ5 ሜትር በፊት መተከል አለባቸው፡፡
ለምሽት ደግሞ አንፀባራቂ ምልክት ማኖር ያስፈልጋል፡፡ በኮንስትራክሽን ቦታዎች ብዙ ጊዜ አደጋ የሚደርሰው በዝቅተኛ ሰራተኞች ላይ ነው፡፡ ባለሙያዎቹማ አደጋ ሊኖር እንደሚችል ስለሚያውቁ ይጠነቀቃሉ፡፡ ስለዚህ ለአደጋ የተጋለጡትን ሰራተኞች ማስተማርና የአደጋ መከላከያ ቆብ እንዲደፉ፣ ቦት ጫማ እንዲያደርጉና ጓንት እንዲያጠልቁ … ማስገደድ ያስፈልጋል በማለት አቶ ንጋቱ አሳስበዋል፡፡
በጉዳዩ ላይ የመስሪያ ቤታቸው አቋም ምን እንደሆነ የተጠየቁት የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን ሥራ አስኪያጅ ኢ/ር ፍቃዱ ኃይሌ፣የሚያስተዳድሩት መስሪያ ቤት የከተማዋን መንገድ የሚሰራና የሚያስተዳድር እንደመሆኑ መሰል አደጋዎች ሲደርሱ ተጠያቂ የማይሆንበት ምክንያት እንደሌለ ይገልፃሉ፡፡
መንገድ ላይ ያሉ ጉዳዮችን እየተከታተለ መዝጋትና መድፈን የባለስልጣኑ ድርሻ ከመሆኑም በላይ ህብረተሰቡም ጥቆማ በመስጠት ሊተባበር ይገባል ያሉት ኢንጂነሩ፤ እስካሁን ወደ መስሪያቤታቸው “ጉዳት ደርሶብኛልና ካሳ ይገባኛል” የሚል አቤቱታ ይዞ የቀረበ ተጎጂ ባይኖርም እንዲህ ያለ አቤቱታ ከቀረበ መስሪያቤታቸው ኢንሹራንስ ገብቶም ቢሆን ማሳከም እንዳለበትና ተጠያቂ መሆን እንደሚችል ተናግረዋል፡፡
መንገድ ሲሰራ ከሰዎች ንክኪ ተከልሎ መሆን እንዳለበት የሚያስገነዝቡት ኢ/ር ፍቃዱ፤ ከዚህ አግባብ ውጪ የመንገድ ግንባታ ሲከናወን አደጋውን ያደረሰው ሥራ ተቋራጭ ከሆነ ባለስልጣኑ ተጠያቂ ይሆናል፡፡ አንዳንድ ተሽከርካሪዎች በእግረኛ መንገድ ላይ ወጥተው የፍሳሽ ማስተላለፊያ ቱቦ ክዳኖችን መስበራቸው ለጉድጓዶቹ መፈጠር መንስኤ ነው ያሉት ኃላፊው፤ በቀለበት መንገድ ላይ ያሉ የፍሳሽ ማስወገጃ ቱቦ የብረት ክዳኖችም በሌቦች መዘረፋቸው ለባለስልጣን መስሪያቤቱ ፈታኝ እየሆነ መምጣቱን ገልጸዋል፡፡ በዚህ ምክንያት ተሽከርካሪዎችና እግረኞች በጉድጓድ እየገቡ ከፍተኛ አደጋ እየደረሰባቸው እንደሚገኝ መረጃው አለን ያሉት ኢ/ር ፍቃዱ፤ ተጠያቂነትን የሚያሰፍን ጠንካራ የህግ አፈፃፀም ያስፈልጋል፤ ኅብረተሰቡም ጉድጓዶች ሲያጋጥሙት ለባለስልጣኑ መጠቆም አለበት ብለዋል፡፡
ችግሩን ለመቅረፍ የባለስልጣን መስሪያቤቱ ሰራተኞች የቱቦ ክዳኖችን ከፍተው ቆሻሻ ካፀዱ በኋላ በአፋጣኝ መልሰው እንዲደፍኑ፣ ኮንትራክተሮችም መንገድ ሲሰሩ ከልለው እንዲሰሩ ጥብቅ ትዕዛዝ እየተላለፈ መሆኑን ኢ/ሩ ገልፀዋል፡፡
ስሜ አይጠቀስ ያሉ አንድ የሕግ ባለሙያ፤ መንገድም ይሁን ህንፃ በአጠቃላይ የመሰረተ ልማት መዋቅር ሲሰራ በሰዎች ደህንነትና አካል ላይ ጉዳት በማያደርስ መልኩ መሆን እንዳለበት የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ እንደሚደነግግ ጠቅሰው፤ የግንባታ ስራው ተጠናቅቆ አገልግሎት በመስጠት ላይ ባለ መንገድ ላይ ለሚደርስ ጉዳት የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣንና የኢትዮጵያ መንገዶች ባለስልጣን፣አደጋው የደረሰበት መንገድ ተጠቅሶ ክስ ሊቀርብባቸው ይችላል ብለዋል፡፡
በኮንስትራክሽን ሂደት ላይ ባለ መንገድ ውስጥ የደረሰ አደጋ ካጋጠመ ግን፣ ተጎጂው መንገዱን የሚያሠራውን ባለስልጣን መስሪያቤትና ሥራ ተቋራጩን በአንድነት በመጥቀስ ኃላፊነት ሊወስድ የሚገባውን አካል ፍ/ቤት ይወስንልኝ ብሎ ክስ ሊመሰርት እንደሚችል ባለሙያው አብራርተዋል። ይህ የክስ አቀራረብ ተመራጭ የሆነው፤ ሥራ ተቋራጩን መቆጣጠር ያለበት አሠሪው መስሪያ ቤት ስለሆነና በመካከላቸው ያለው ውል ስለማይታወቅ ነው ብለዋል፤ ባለሙያው፡፡
በእኛ ሀገር እንደ ልማድ ሆኖ መንገድ ሲሰራ የጥንቃቄ ምልክቶች እንደማይቀመጡ መታዘባቸውን የተናገሩት ባለሙያው፤ በአንዳንድ የሰለጠኑ ሀገሮች ከ5 ሜትር ርቀት ላይ ምልክቶችና አቅጣጫዎች እንደሚቀመጡ በመጠቆም በእኛም ሀገር ይህ አስገዳጅ ህግ ተፈፃሚ መደረግ አለበት ሲሉ ይመክራሉ፡፡ በቴሌ ኬብል ቀበራ ወቅት ጉድጓዶች ሳይከደኑ ከቀሩም የቴሌ መሆኑን በማረጋገጥ፣ አሊያም ፍ/ቤት ያጣራልኝ በማለት የመንገዶች ባለስልጣንና ቴሌን አጣምሮ ክስ መመስረት ይቻላል ብለዋል፡፡
በእኛ ሀገር የመንግሥት መስሪያ ቤቶችን በወንጀል መክሰስ (ኮርፖሬት ክሪሚናል ሊያቢሊቲ) በሚለው ፅንሰ ሐሳብ መነሻነት የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ እንደሚከለክል የጠቆሙት የህግ ባለሙያው፤ ተጎጂው የደረሰበትን የጉዳት መጠን ጠቅሶ “ልካስ ይገባኛል” ብሎ የፍትሐብሔር ክስ ማቅረብ ይችላል ብለዋል፡፡ “መንግሥትን ከስሼ ካሣ አገኛለሁ” የሚለው ሐሳብ በራሱ በኛ ሀገር ካለመለመዱም በላይ በፍ/ቤቶች የተንዛዛ አሰራር ምክንያት ተጎጂዎች መብታቸውን እንዳያስከብሩ ዳተኛ ያደርጋል ያሉት ባለሙያው፤ ይህ ባህል መቀረፍ እንዳለበትና ሰዎች ሕጉ የሰጣቸውን መብት እንዲያስከብሩ አሳስበዋል።  
በጉዳዩ ላይ የሚመለከታቸውን የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ አገልግሎት እና የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን መስሪያ ቤትን አስተያየት ለማካተት ያደረግነው ሙከራ ስልካቸው ባለመነሣቱ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡          

Published in ዜና

የፕሬዚዳንት ጽ/ቤት ሃላፊ የነበሩት ወ/ሮ አማረች በቃሉ፤ከቀድሞ ፕሬዚዳንት አቶ ግርማ ወልደጊዮርጊስ የቤት ኪራይ ውል አፈፃፀም ጋር በተገናኘ በተፈጠረ የሥራ ዝርክርክነት  ከሃላፊነታቸው እንደተነሱ ምንጮች ጠቆሙ፡፡
መጋቢት 11 ቀን 2006 ዓ.ም በጠቅላይ ሚኒስትሩ በተፃፈ ደብዳቤ ሃላፊዋ፣ በአሰራር ዝርክርክነት ከሃላፊነታቸው እንደተነሱ የጠቆሙት ምንጮች፤በዝርክርክነት ተብሎ የተጠቀሰውም የቀድሞ ፕሬዚዳንት የቤት ኪራይ ውል አፈፃፀም እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ወ/ሮ አማረች ግን ይሄን አይቀበሉም፡፡ ጉዳዩ በኢህአዴግ የተለመደ የስራ ዝውውር እንጂ የአሠራር ዝርክርክነትም ሆነ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ጉዳይን የተመለከተ አይደለም ሲሉ አስተባብለዋል፡፡ ምንጮች እንደሚሉት፤ ከአንድ ወር በፊት በፅ/ቤቱ በተደረገ ግምገማ በጽ/ቤቱ የአመራር፣ የአስተዳደርና  የአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ዝርክርክነት እንዳለ የተጠቀሰ ሲሆን ወ/ሮ አማረችም በተመሳሳይ ጉዳይ ተገምግመዋል፡፡
ከግምገማው ጋር ግንኙነት እንዳለው ባይታወቅም አዲሱ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ባለፈው ጥር ወር ላይ በፃፉት ደብዳቤ፤ የፅ/ቤቱ ሃላፊ ወ/ሮ አማረች በቃሉ ከሃላፊነታቸው እንዲነሱላቸው ጠይቀው እንደነበር ምንጮች አስታውሰው፤ ሃላፊዋ ላለፉት ሶስት ወራት በሥራቸው ላይ ቆይተው በዚህ ወር ከሃላፊነታቸው እንደተነሱ ገልፀዋል፡፡
ከሃላፊነታቸው በተነሱት ወ/ሮ አማረች በቃሉ ምትክም የአዲስ አበባ ከንቲባ ጽ/ቤት ሃላፊ የነበሩት አቶ ብሩክ ግዛው የተሾሙ ሲሆን ስለአዲሱ ኃላፊነታቸው የጠይቀናቸው አቶ ብሩክ፣መልስ ከመስጠት ተቆጥበዋል፡፡
የቀድሞው ፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ አሁን የተከራዩትን መኖርያ ቤት አፈላልጎ ያገኘላቸው የኮሚሽን ሰራተኛ፣በውሉ መሰረት ክፍያ አልተፈፀመልኝም በማለት በፕሬዚዳንቱ ፅ/ቤት፣ በፕሬዚዳንቱና በልጃቸው ላይ ክስ መመስረቱ የሚታወቅ ሲሆን መጀመርያ ላይ ቤት ያከራየው ግለሰብም ከፕሬዚዳንቱ ፅ/ቤት የ2.1 ሚ ብር ካሣ እንዲከፈለው የመጨረሻ የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ በማስገባት ቀጣዩ እርምጃ ክስ መመስረት እንደሆነ ተናግሯል፡፡
ምንጮች እንደሚሉት፤ ይሄ ሁሉ ችግር የተፈጠረው በፕሬዚዳንቱ ፅ/ቤት የአመራርና አስተዳደር እንዝላልነት ሲሆን የሃላፊዋ መነሳትም ከዚህ ጋር በቀጥታ የተገናኘ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡

Published in ዜና

“ወደ አንድነት ፓርቲ የመጣነው መሬት ያስመልስልናል ብለን አይደለም”
 ስምንቱ በአዲስ አበባ ከተማ ክፍለ ከተማ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው አድረዋል  
“ያለ አግባብ የተያዘ መሬት ላይ ሁሌም እግድ ይጣላል” - የዞኑ አስተዳደር
በኦሮሚያ ክልል በምዕራብ ሸዋ ዞን ዳኖ ወረዳ አዋዲ ጉልፋ ቀበሌ፤ የመጡ 29 የአማራ ተወላጅ አርሶ አደሮች “መሬት እንዳናርስ ተከለከልን፤ ቅሬታችንን የሚሰማን አጣን” ሲሉ አማረሩ፡፡ ከ29ኙ ስምንቱ በአዲስ ከተማ ክ/ከተማ፣ ወረዳ ሰባት ፖሊስ ጣቢያ፣ ረቡዕ ማታ ታስረው ማደራቸውንና ሀሙስ ረፋድ ላይ መለቀቃቸውን አርሶ አደሮቹ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ አርሶ አደሮቹ አብዛኞቹ ከ1986 ዓ.ም ጀምሮ ከጎንደርና ከሌሎች የአማራ አካባቢዎች መሸኛ በማምጣት መሬት እንደተሰጣቸው፣ በአዋዲ ጉልፋ፣ በአጂላ ዳሌና በዙሪያው መሬት በማልማት፣ ቤተእምነት በመገንባትና ሌሎት መሰረተ ልማቶችን በመስራት ከ20 ዓመታት በላይ በሰላም እንደኖሩ ገልፀው፣ ከ2004 ዓ.ም ወዲህ ግን በአማራ ተወላጅ አርሶ አደሮች ላይ የመሬት እቀባ እንደተጣለ ተናግረዋል፡፡
አቶ ቢያዝን አበራ የ65 ዓመት አዛውንት ናቸው። ትውልድና እድገታቸው ጎንደር ቢሆንም በመሬት ጥበትና በተፈጥሮ መጎዳት ሳቢያ ወደ ምዕራብ ሸዋ ዞን ዳኖ ወረዳ አዋዲ ጎልፋ ቀበሌ በ1986 ዓ.ም መጥተው መኖር እንደጀመሩ ይናገራሉ፡፡ ላለፉት 20 ዓመታት መሬታቸውን እያረሱ፣ ለመሰረተ ልማት መዋጮ እያዋጡ፣ አካባቢያቸውን እያለሙ ዘጠኝ ልጆቻውን ሲያሳድጉ መኖራቸውን ገልፀዋል፡፡ ይሁን እንጂ ከ2004 ዓ.ም በኋላ ነገሮች እየተቀየሩ፣ የአካባቢው ባለስልጣናት ባህሪ እየተለወጠና በአማራ ተወላጆች ላይ ጫናው እየበረታ እንደመጣ ገልፀዋል፡፡ “በ2004 ዓ.ም የአማራ ህዝብ ከሰፈረባቸው ቀበሌዎች አንዱ በሆነው አጂላዳሌ ቀበሌ፣ ከሰሜን ሸዋ የመጡ የ150 አባወራዎች ቤት በእሳት ጋይቶ ሰዎቹ የት እንደደረሱ ጠፍተዋል” ያሉት አቶ ቢያዝን፤እርሳቸው በሚኖሩበት አዋዲ ጉልፋ ቀበሌም “ለአማራ ተወላጆች ሁለት ሁለት ሄክታር መሬት ይበቃል፤ ቀሪውን ለኦሮሚያ ወጣቶች እንሰጣለን” በሚል መሬታቸውን አርሰው እንዳይበሉ እንዳደረጉዋቸው ተናግረዋል፡፡ “ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ከወረዳ ወደ ዞን፣ ከዞን ወደ ክልል አቤት ብለን ሰሚ በማጣታችን ወደ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽ/ቤት እና ወደ ፌዴሬሽን ም/ቤት አቤት ብለናል” ያሉት አዛውንቱ፤ “ይህን የሚያደርገው የአስተሳሰብ እጥረት ያለበት ነው፤ ወደ ቦታችሁ ተመለሱ ውሳኔ እንሰጣለን” ብንባልም እስካሁን ምንም ውሳኔ አላገኘንም ብለዋል፡፡ “ጉዳዩ በእንጥልጥል እያለ መጋቢት 8 ቀን 2006 ዓ.ም አንድም በአማራ ተወላጆች የተያዘ መሬት እንዳይታረስና እንዳይዘራ የሚል እግድ ደብዳቤ ወጣብን” በማለት የእግድ ደብዳቤውን በማስረጃነት አቅርበዋል፡፡
ደሳለኝ በላቸው የተባሉት ሌላው የ43 ዓመት ጎልማሳ፤ ከ1978 ዓ.ም ጀምሮ ከአባታቸው ጋር ወደ ናኖ ወረዳ እንደመጡ ገልፀው፣ ከናኖ ወደ ዳኖ የመጡበት ምክንያት በወረዳው ሰዎች በተደረገላቸው የአብረን እንኑር ጥሪ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ ከደቡብ ጎንደር በልጅነታቸው እንደመጡ የገለፁት አቶ ደሳለኝ፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ስምንት ልጆችን አፍርተው በሰላም መኖር እንደ ጀመሩ ገልፀዋል፡፡ ከ29ኙ የአማራ ተወላጅ አርሶ አደሮች ጋር በአንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ ቢሮ ውስጥ በተነጠፈ ጂባ ላይ ተቀምጠው ያገኘናቸው ጎልማሳው፤ በወረዳው ባለስልጣናት ከፍተኛ የመብት ጥሰት እየደረሰ እንደሆነ ገልጸው በአካባቢው ያሉ የመኪና መንገዶችን፣ ቤተ እምነቶችን እና መሰል መሰረተ ልማቶችን ከመሰሎቻቸው ጋር መገንባታቸውን፣ ጠፍ የነበረውን መሬት አልምተው ግብር እየከፈሉ፣ ለመሰረተ ልማትና ለአባይ ግድብ እንደ ማንኛውም ዜጋ እያዋጡ እየኖሩ “አማራ ነህ ፤መሬት አይገባህም” መባላቸውን ተቃውመዋል፡፡
“ትምህርት የሚሰጠው በኦሮምኛ ብቻ በመሆኑ ልጆቻችንን ወሊሶና ወልቂጤ ልከን በስንቅ እናስተምራለን” ያሉት አቶ ደሳለኝ፤ “በወረዳውና በቀበሌው ኃላፊዎች ስብሰባ ተጠርተን ሄደን በኦሮምኛ ተጀምሮ በኦሮምኛ ያልቃል፤ ስብሰባው እኛን የማያሳትፍ ከሆነ ለምን ጠራችሁን ስንል፤ ግዴታችሁ ነው እንባላለን” ብለዋል፡፡
“ይባስ ብለው መሬት ለምን ትቀሙናላችሁ? አብረናችሁ የኖርን፣ አካባቢውን ያለማን ነን ስንል ድብደባና ግርፋት ደርሶብናል” ያሉት አቶ ደሳለኝ፤ በዚህ ሳቢያ ጌጡ ክብረት የተባለ የአጂላ ፉዳሌ ቀበሌ ነዋሪ የአማራ ተወላጅ፣ህግና ፖሊስ ባለበት ተደብድቦ ሞቷል፤ እስካሁን ገዳዮቹም አልተያዙም፤ ክስም አልተመሰረተም” ሲሉ አማረዋል፡፡ ከ20 ዓመት በላይ ኖረን ጥሩ ልማትና ጥሩ ስራ ስንሰራ “ህገ-ወጥ ሰፋሪዎች ናችሁ፤ ወደ ክልላችሁ ሂዱ፤ መሬቱ ለኦሮሞ ወጣቶች ይፈለጋል” ተባልን ያሉት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፤ ይሄም ኢትዮጵያዊነታችንን እንድንጠራጠር አድርጎናል ብለዋል፡፡
ለፌዴሬሽን ም/ቤት በተደጋጋሚ አቤት ማለታቸውንና ምላሽ አለማግኘታቸውን የገለፁት አርሶ አደሮቹ፤ በድጋሚም መምጣታቸውን ጠቁመው፤ “የፌዴሬሽን ም/ቤት አፈጉባኤ ስለሌሉ ወደ ቦታችሁ ተመለሱ” የሚል ምላሽ እንደተሰጣቸው ተናግረዋል፡፡ የመጣችሁት ፌዴሬሽን ም/ቤት ከሆነ እንዴት ወደ አንድነት ፓርቲ ጽ/ቤት መጣችሁ በማለት ላቀረብነው ጥያቄም፤ “በአገሪቱ መሪ በኢህአዴጋችን ምላሽ በማጣታችን ጉዳያችንን ለኢትዮጵያ እና ለዓለም ሚዲያ እንዲያሰሙልን በሚል ነው የመጣነው” ብለዋል አቶ ደሳለኝ፡፡ በአሁኑ ሰዓት በአማራ ተወላጅ አርሶ አደሮች ላይ በአካባቢው ባለስልጣናት እየደረሰ ያለው ግፍና በደል ቆሞ፣ መሬታቸውን እንዳያርሱ የተጣለው እግድ ተነስቶ፣ በሰላም መኖር እንደሚፈልጉ የገለፁት አርሶ አደሮቹ፤ይህ ምላሽ የሚገኘውም ከገዢው ፓርቲ እንደሆነ በመጠቆም አስቸኳይ እርምጃ እንዲወሰድላቸው ተማፅነዋል፡፡
“ወደ አንድነት ፓርቲ የመጣነው መሬት ያስመልስልናል ብለን አይደለም” ያሉት ሌላው አርሶ አደር፤ በመንግስት በኩል ምላሽ አጥተን መተንፈሻ በማጣታችን ነው ብለዋል፡፡ “የትኛውንም የአካባቢው ተወላጆች የሚያደርጉትን መዋጮ ለአባይ ግድብ፣ ለመንገድ ስራ እያዋጣንና ግብር እየከፈልን ባለበት መሬት እንዳናርስ የታገድንበት ሁኔታ አሳዝኖናል፤ ዜግነታችንና ህልውናችን አደጋ ላይ ወድቋል፤ መንግስት አስቸኳይ መፍትሄ ይስጠን” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ “አሁን ያላችሁበት አካባቢ አትኖሩም ከተባልንም መንግስት ሌላ የምንኖርበት ቦታ ወስዶ እንዲያሰፍረን እንጠይቃለን” ብለዋል፡፡
“በአሁኑ ሰዓት ሰሚ አጥን ስንከራተት የአንድነት ፓርቲ አመራሮች ተቀብለው ምግብ እና መኝታ እንድናገኝ አድረገውናል፤ ያለ ስንቅ ነበር የመጣነው” ብለዋል፤አርሶአደሮቹ፡፡ ጉዳያቸውን ለጋዜጠኞች አስረድተው ወደ አገራቸው ሲመለሱ፣ አውቶቡስ ተራ አካባቢ ፖሊሶች ለጥያቄ እንፈልጋችኋለን በማለት ቢያዝን አበራ፣ ደሳለኝ በላቸው፣ ኑሮዬ እንድሪስ፣ ፀጋ ዳምጠውና ሌሎች አራት ሰዎችን በአዲስ ከተማ ክ/ከተማ ወረዳ ሰባት ፖሊስ ጣቢያ እንደወሰዷቸው የገለፁት አርሶ አደሮች፤ ለምን መጣችሁ፣ ወደ አንድነት ፓርቲ የመራችሁ ማን ነው፣ ከየት ነው የመጣችሁት እና ሌሎች ጥያቄዎች ቀርቦላቸው  መልስ ከሰጡ በኋላ፣ ፖሊስ ጣቢያ አድረው ሀሙስ 3፡30 መለቀቃቸውን  ገልፀዋል፡፡
የምዕራብ ሸዋ ዞን መስተዳድር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ቱፋ ቴሶ በበኩላቸው፤ በአማራ ተወላጆች ላይ ደርሷል የተባለውን በደል እንደማያውቁት ገልፀው፣ ችግሮችም ካሉ ለዞኑ ማመልከትና ተበድለናል ያሉት አርሶ አደሮች ተሳታፊ በሆኑበት መንገድ ተወያይቶ መፍታት ይቻል እንደነበር ተናግረዋል፡፡ “ችግሩ ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ እንዳለ አላውቅም፣ ወደ ኃላፊነቱ የመጣሁት በቅርብ ነው” ያሉት አቶ ቱፋ፤ ችግራቸውን በተዋረድ ሳያሰሙ ወደ ፌዴሬሽን ም/ቤት መሄዳቸው አግባብ እንዳልሆነና ለዞኑ ያሰሙት ቅሬታ እንደሌለ ተናግረዋል፡፡ “እኛ አማራ ቢሆኑም ከየትኛውም ብሔር ቢመጡም የምናያቸው በወንድምነት ነው“ ያሉት የመስተዳድሩ ጽ/ቤት ኃላፊ፤ አሁንም ቢሆን ችግራቸውን ቀርበው ያወያዩንና በስፍራው ተገኝተን ከወረዳው ኃላፊዎች ጋር ተመካክረን እንፈታዋለን” ብለዋል፡፡
የአማራ አርሶ አደሮች፣ልጆቻችን በአማርኛ ቋንቋ መማር አልቻሉም በማለት ባነሱት ቅሬታ ዙሪያ አቶ ቱፋ ሲመልሱ፤ “በአገር አቀፍ ደረጃ ከአንድ ክልል መጥተው ሌላ ክልል ውስጥ ለሚኖሩ ዜጎች ት/ቤት ተከፍቶ በልዩ ሁኔታ በአፍ መፍቻ ቋንቋቸው እንዲማሩ እየተደረገ ነው፡፡ በአጠቃላይ ግን ያለባቸውን ቅሬታ ከዞኑ መስተዳድር ጋር መነጋገር ይኖርባቸዋል” ካሉ በኋላ፣ከዳኖ ወረዳ ወደ ፌደራል መንግስት ቅሬታ ለማሰማት የሄዱ የአማራ አርሶ አደሮች መኖራቸውን የሰሙት በወሬ ደረጃ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
“አርሶ አደሮቹ ከአካባቢው ተወላጅ ተለይተው የሚታዩበት መንገድ የለም” ያሉት አቶ ቱፋ፤ ከመጠን በላይ የያዙት መሬት ካለም ሆነ ያለአግባብ ታግደውና መሬት ተወስዶባቸው ከሆነ፣ ሁሉም በህግና በስርዓት እንደሚታይ ገልፀው፤ ከህግ በላይ የሚሆን ማንም እንደሌለ ተናግረዋል፡፡  
የዞኑ ምክትል መስተዳድር አቶ ከሳዬ ገመቹ በበኩላቸው፤ “የታገደ መሬት ካለም ያለ አግባብና በህገ-ወጥ መንገድ የተያዘ ነው” ካሉ በኋላ ከዚህ ቀደም በዚህ ጉዳይ ቅሬታ ያነሱ ሰዎች እንደነበሩና በዞን፣ በወረዳ፣ በክልል እና ከእምባ ጠባቂ ተቋም ተወካዮች መጥተው ጉዳዩ ውሳኔ አግኝቷል ብለዋል፡፡
በአማራም ሆነ በአካባቢው ተወላጆች ያለአግባብና ከመጠን በላይ የተያዘ ካለ ታይቶ መሬት ለሌለው ይሰጣል፤ የተረፈው ወደ መንግስት የመሬት ባንክ ይገባል ያሉት ምክትል መስተዳድሩ፤ “በህገ-ወጥ መንገድ ያልተፈቀደ መሬት ይዘው ከአማራ ክልል ስለመጡ የተበደሉ አድርገው ማቅረባቸው፣ህዝብን ከህዝብ ለማጋጨትና ለመከፋፈል ሆነ ብለው የሚያደርጉት ነው ብለዋል፡፡

Published in ዜና

      አዲስ ትውልድ ፓርቲ (አትፓ) የተቃዋሚ ፓርቲዎች ብሔራዊ ጉባዔ በቅርቡ ለማካሄድ ያቀደ ሲሆን ተቃዋሚዎች ልዩነታቸውን አቻችለው ጠንካራ ስብስብስ መፍጠር እንደሚችሉ እምነቱን ገልፆ አገር አቀፍ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጉባኤው ላይ እንዲሳተፉ ጥሪውን አቅርቧል፡፡ ፓርቲው ሚያዚያ 30  የተቃዋሚ ፓርቲዎች ብሄራዊ  ቀን ተብሎ እንዲሰየምም ጠይቋል፡፡
በጉባኤው ላይ ተቃዋሚዎች በህብረት፣ በጥምረትና በቅንጅት ለመሥራት ያልቻሉባቸው ምክንያቶች እንደሚፈተሹ የጠቆመው ፓርቲው፤ ልዩነቶችን በማጥበብ ጠንካራ የተቃዋሚዎች ስብስብ መፍጠር ይቻላል ብሎ እንደሚያምን  ገልጿል። ከተመሠረተ ጥቂት ዓመታትን ያስቆጠረው አዲስ ትውልድ ፓርቲ፤   ተቃዋሚዎች ልዩነቶችን በማቻቻል በቀጣዩ ዓመት በሚካሄደው አገራዊ ምርጫ፣ የኢትዮጵያን ህዝብ ጥያቄ ለመመለስ ይችሉ ዘንድ ለ23 ዓመታት ሊፈጥሩት ያልቻሉትን ጠንካራና አማካይ የተቃዋሚዎች ስብስብ ለመፍጠር ማለሙን አስታውቋል፡፡
በተቃዋሚ ፓርቲዎች ብሔራዊ ጉባዔው ላይ 21 በሚደርሱ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ ፅሑፎች እንደሚቀርቡ የጠቆመው አዲስ ትውልድ ፓርቲ፤ ከርእሰ ጉዳዮቹም መካከል “የተሳካና የሰለጠነ የተቃውሞ ፖለቲካ የትግል ስልት እንዴት ይመጣል?”፣ “በኢትዮጵያ ብሄራዊ እርቅና መግባባት እንዴት፣ መቼና የት ይካሄዳል?”፣ “ዲሞክራሲያዊ የመንግስት ለውጥና ሽግግር በኢትዮጵያ መቼና እንዴት ይካሄዳል?”፣ “በኢትዮጵያ ለተቃውሞ ትግል ስኬት የሚበጀው አንድ ጠንካራ ውህድ ፓርቲ? ወይስ የፓርቲዎች ህብረት? ግንባር ወይስ ቅንጅት?” የሚሉት ይገኙበታል፡፡ በጉባኤው ላይ የሚሳተፉ የፖለቲካ ፓርቲዎች በርእሰ ጉዳዮቹ ላይ ጥናታዊ ፅሁፎችን ማቅረብ እንደሚችሉ የገለፀው ፓርቲው፤ በአገር ውስጥና በውጭ አገር የሚገኙ ምሁራንም ጥናታዊ ፅሁፎችን እንዲያቀርቡ  ጋብዟል፡፡
አዲስ ትውልድ ፓርቲ፤ ለ22 አገር አቀፍ ፓርቲዎች የውይይት ጥሪ ያቀረበ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ  የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዲሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ(መድረክ)፣ አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ(አንድነት)፣ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት(መኢአድ) እና ሰማያዊ ፓርቲ እንደሚገኙበት ለማወቅ ተችሏል፡፡

Published in ዜና

          ለውይይት ወደ ወላይታ ሶዶ ሄደው የነበሩት የአንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ አመራሮች  ከፍተኛ እንግልትና የንብረት ውድመት እንደደረሰባቸው ገለፁ፡፡ የፓርቲው የድርጅት ጉዳይ ሃላፊና ምክትል የድርጅት ጉዳይ ሃላፊውን ጨምሮ  የፓርቲው የወረዳው አመራሮች ተንቀሳቃሽ ስልኮች ባልታወቀ ኬሚካል ተነክረው ከጥቅም ውጭ መደረጋቸውን የአንድነት ፓርቲ አመራር  አቶ ዳንኤል ተፈራ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ በአንድነት አጠቃላይ እንቅስቃሴና በተሻሻለው የፓርቲው ፕሮግራም ላይ ለመወያየት አቶ ዳንኤል ተፈራና ምክትል የድርጅት ጉዳይ ሃላፊ አቶ ዳንኤል ሺበሺ በተደረገላቸው ጥሪ፣  ወደ ወላይታ ሶዶ ከተማ መጓዛቸውን ገልፀው፣ከቀኑ አምስት ሰዓት አካባቢ በአንዱ የአንድነት አባል መኖርያ ግቢ ውስጥ ቡና እየጠጡ ለመወያየት መወሰናቸውን  ይናገራሉ፤ አቶ ዳንኤል ተፈራ፡፡
በምክትል የድርጅት ጉዳይ ሃላፊው የመግቢያ ንግግር ተደርጐ ውይይቱ ሊጀመር ሲል ከስምንት እስከ አስር የሚጠጉ ሰዎች የግቢውን በር በእርግጫ ሰብረው መግባታቸውን ያስታወሱት ሃላፊው፤ሰዎቹ በቀጥታ ፊት ለፊት ያገኙትን እቃ መሰብሰብ መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ እነዚህ ሰዎች ታርጋ በሌላቸው ሞተርሳይክሎች እንደመጡ የተናገሩት አቶ ዳንኤል፤ማንነታቸውን እንዳልገለፁ፣ ምን እየሰሩ እንደነበር  አለመጠየቃቸውንና ምን እንደሚፈልጉ አለማሳወቃቸውን ገልፀው፤ እጃቸው ላይ የነበረውን የአንድነት ፓርቲ ፕሮግራም፣ የግል ማስታወሻ ደብተራቸውን፣በአጠቃላይ ፊት ለፊት ያገኟቸውን ንብረቶች ሰብስበው እንደወሰዱ ጠቁመዋል፡፡ በተለይም የድርጅት ጉዳይ ምክትል ሃላፊውን 16ሺህ ብር የሚያወጣ ተንቀሳቃሽ ስልክ አንገቱን በከረባቱ በማነቅ እንደወሰዱበት አቶ ዳንኤል እማኝነታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ንብረቱን የወሰዱት አራት ሰዎች ቀድመው ሲሄዱ፣ ሌሎቹ አራቱ አብረዋቸው እንደቀሩ ያስታወሱት አቶ ዳንኤል፤ ህገ ወጥ ስብሰባ ስላደረጋችሁ ፖሊስ ይምጣና ወደ ጣቢያ ትሄዳላችሁ እንዳሏቸው ገልፀው፣ በኋላም ከፖሊሶች ጋር ወደከተማው ፖሊስ ጣቢያ መሄዳቸውን ይገልፃሉ፡፡
“ፖሊስ ጣቢያ እንደደረስን የወላይታ ከተማ ፖሊስ አዛዥ የሆኑትን ሻለቃ ላሊሼ አሌን አገኘናቸው” ያሉት አቶ ዳንኤል ተፈራ፤ፖሊስ ለምን አመጣሃቸው ተብሎ ሲጠየቅ “ህገ-ወጥ ስብሰባ ሲያደርጉ አገኘኋቸው” የሚል ምላሽ እንደሰጠ ተናግረዋል፡፡
“በኋላም ሞባይላችሁን ፊት ለፊት ቁጭ አድርጉ ተብለን፣የፖሊስ አዛዡን በማመንና ህግ አስከባሪነታቸውን በመቀበል የታዘዝነውን አደረግን” ያሉት አቶ ዳንኤል፤ወደ ሌላ ክፍል ተወስደው እስከ ሌሊቱ ስድስት ሰዓት መቆየታቸውን ተናግረዋል፡፡ “ልክ ከሌሊቱ ስድስት ሰዓት ላይ የከተማው መብራት ጠፋ፤ ይሄኔ የእኔና የሌሎች 20 የአንድነት የወረዳ አመራሮች ስልክ ባልታወቀ ፈሳሽ ኬሚካል ተነክሮና በአረፋ ተጥለቅልቆ ተሰጠን” ያሉት አቶ ዳንኤል፤ ስድስት ሰዓት ላይ ውጡ ሲባሉ ለደህንነታቸው ሰግተው ላለመሄድ አመንትተው እንደነበር፤ ነገር ግን ፖሊስ ጣቢያውም የበለጠ ስለሚያስፈራ ወጥተው ወደያዙት መኝታ መሄዳቸውን ገልፀዋል፡፡ የሁሉም ሞባይል ስልክ ከጥቅም ውጭ ሆኖ እንደመጣ ጠቁመው፣ ባለ 16 ሺህ ብሩ የአቶ ዳንኤል ሺበሺ ሞባይል ስልክ ግን ከእነአካቴው እንዳልተመለሰ ተናግረዋል፡፡ “እኛ ህጋዊና በህጋዊ መንገድ የምንቀሳቀስ የፓርቲ አመራሮችና አባላት ብንሆንም በከተማው ህገ ወጥ ሰዎች የደረሰብን እንግልት፣ እስራትና የንብረት ውድመት አሳፋሪ ነው” ሲሉ አቶ ዳንኤል አውግዘውታል፡፡
“ህገወጥ ስብሰባ አላደረግንም፣ ልንወያይ የነበረው በአጠቃላይ በዞኑ የፓርቲው እንቅስቃሴ፣ በተሻሻለው የአንድነት ፕሮግራምና በአካባቢው ያሉ የአንድነት አባላትና አመራሮች ለ2007ቱ ምርጫ በገንዘብም ሆነ በእውቀት አቅማቸውን እንዴት ይገንቡ በሚለው ጉዳይ ላይ ነው” ያሉት አቶ ዳንኤል፤ ህገወጥ ስብሰባ አደረጉ በሚል ባልዋልንበት አውለውናል ብለዋል፡፡ “ህጋዊ ስብሰባ ማድረግ እየቻልን እንዴት ህገወጥ ስብሰባ እናደርጋለን?” ሲሉም የአንድነት የድርጅት ጉዳይ ሃላፊ ዳንኤል ተፈራ ጠይቀዋል፡፡   
ጉዳዩን በተመለከተ በስልክ ምላሽ እንዲሰጡን የጠየቅናቸው የወላይታ ሶዶ ከተማ ፖሊስ አዛዥ ሻለቃ ላሊሼ ኦሌ፤ ለምን ጉዳይ እንደምንፈልጋቸው ጠይቀውን ከነገርናቸው በኋላ “አሁን ስብሰባ ላይ ነኝ፤ ስጨርስ እደውላለሁ” ብለውን ነበር፡፡ እሳቸው ባለመደወላቸው እኛ ደጋግመን የደወልን ቢሆንም ስልካቸውን ባለማንሳታቸው ምላሻቸውን ለማካተት ያደረግነው ጥረት ሳይሳካ ቀርቷል፡፡  

Published in ዜና

“አፉን ከወጋኸውማ አሰፋኸው!”
(የጐንቸ ኤትወኸተታ ወካዀንም ቢውሪ አንቃታ ባረም፣
አንቃሸታ ቦካዀ አቤተትዀንም) - የጉራጊኛ ተረት

በዩናይትድ ስቴትስ እንደቀልድ የሚወራ ዛሬ ተረት የሆነ አንድ ትርክት አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዝቅ ብሎ የህዝቡን የኑሮ ደረጃ ማየት ወሳኝ ነው በሚል እሳቤ፣ በመጀመሪያ የሴተኛ አዳሪዎችን ህይወት  ሊያዩ ሄዱ፡፡ ሦስት ዓይነት ደረጃ ያላቸው ሴቶችን አገኙ ይባላል፡፡
አንደኛ ደረጃ የምትባለዋ ባለ ወርቃማ ፀጉት ናት፡፡
ሁለተኛ ደረጃ የምትባለው ባለቀይ ፀጉር ናት፡፡
ሦስተኛ ደረጃ የምትባለው ባለጥቁር ፀጉር ናት፡፡ ይቺኛዋ የኑሮ ደረጃዋ የመጨረሻ ዝቅ ያለ ሴት ናት ማለት ነው። በመጀመሪያ አንደኛ ደረጃዋ ዘንድ ይሄዱና፤
“እኔ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ነኝ፡፡ ከአንቺ ጋር አንድ ምሽት ማሳለፍ እፈልጋለሁ፡፡ ምን ያህል ገንዘብ ትጠይቂኛለሽ?” አሏት፡፡
ባለ ወርቃማ ፀጉሯ ሴትም፤
“ሰላሳ ሺ ዶላር ይበቃኛል” አለቻቸው፡፡
“ጥሩ፤ እንግዲህ ዘወር ዘወር ብዬ ሌሎችን አጠያይቄ እመለሳለሁ” ብለው ወደ ሁለተኛ ደረጃዋ ባለ ቀይ ፀጉር ሴተኛ አዳሪ ይሄዳሉ፡፡
ለእሷም፤
“እኔ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ነኝ፡፡ ከአንቺ ጋር አንድ ማታ ማሳለፍና ተዝናንቼ ለማደር ምን ያህል ገንዘብ ይፈጅብኝ ይሆን?” ሲሉ ይጠይቃሉ፡፡
ባለ ቀይ ፀጉራ ሴትም፤
“ሃያ ሺህ ዶላር በቂ ነው ለእኔ” ትላቸዋለች፡፡
ፕሬዚዳንቱም፤
“እስቲ ዘወር ዘወር ብዬ የተሻለ ክፍያ አገኝ እንደሆነ አጠያይቄ እመለሳለሁ፡፡ ይሄ የመጨረሻ ዋጋ መሆኑ ነው አይደለም?”
“አዎን” አለቻቸው ሳታመነታ፡፡ በመጨረሻ ወደ ዝቅተኛዋ ባለጥቁር ፀጉር ሴት ዘንድ ይሄዱና፤
“እኔ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ነኝ፡፡ ከአንቺ ጋር አንድ ቆንጆ ምሽት ለማሳለፍ እፈልጋለሁ፡፡ ምን ያህል ገንዘብ እንደሚያስፈልገኝ ንገሪኝ፡፡ ታዲያ፤ ምንም ሳትፈሪ የሚያዋጣሽን ሀቀኛ የገንዘብ መጠን ነው የምትነግሪኝ እሺ?” አሏት፡፡
ባለ ጥቁር ፀጉርዋ ሴተኛ አዳሪም አውጥታ፣ አውርዳ የሚከተለውን መልስ ሰጠቻቸው፡፡
ስድስት ቅድመ - ሁኔታዎችን ካሟሉ ከእኔ ጋር በነፃ ለማደር ይችላሉ፡፡ ብላ ጀመረች፡፡
ፕሬዚዳንቱም በችኮላ፣
“ምን ምንድናቸው?” ብለው ጠየቋት፡፡ ባለ ጥቁር ፀጉሩዋ ሴትም፤
“አይቸኩሉ፤ ልነግርዎት ነው፡፡ ደግሞም እርሶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሲሰጡ እንደሚያስረዝሙት አላንዛዛውም፡፡”
1ኛ/ ቀሚሴን በጣም ከፍ የሚያደርጉት የሚያስከፍሉኝን ቀረጥ ያህል ለመሆን ከቻለ፤
2ኛ/ የውስጥ ሱሪዬን ዝቅ የሚያደርጉት የሰራተኛው ህዝብ ዝቅተኛ ደሞዝ ድረስ ከሆነ፤
3ኛ/ የሰውነትዎ ጥንካሬ እንደ ኑሮ የከበደ ከሆነ፣
4ኛ/ በዚሁ ከባድና ጠንካራ ሁኔታ እኔ ለዳቦ ስሰለፍ የምቆመውን ያህል ጊዜ፤ ጠንክረው የሚቆዩ ከሆነ፤
5ኛ/ እቅፍዎ ውስጥ ሲያስገቡኝ፤ ከምኖርበት በክረምት ብርድ የተሞላ ቤት የተሻለ የሚሞቀኝ ከሆነ
6ኛ/ የፍቅር ጨዋታዎ ህዝቡን የሚጫወቱበትን ዓይነት ከሆነ፤ ነው፡፡ ዕውነቴን ነው የምልዎት አምስት ሳንቲም ሳይከፍሉ ከእኔ ጋር በነፃ ማደር ይችላሉ” አለቻቸው፡፡
*     *      *
የህዝብን የኑሮ ደረጃ ዝቅ ብሎ ወርዶ የሚያይ መሪ፣ አለቃ፣ ኃላፊ ማግኘት መታደል ነው፡፡ ያስቀናል፡፡ የዋጋ መናርና የታክስ ማሻቀብ አንድን ማህበረሰብ የጦርነትን ያህል ያጠፋዋል፡፡ ለዚህ ነው መሪዎች ሁሉ የህዝባቸውን ኑሮ በቅርብ ያስተውሉ የሚባለው፡፡ ህዝብ የሀገር ሙቀት መለኪያ ነው፡፡ ህዝብ የሚከፍለው ግብር ከሚያገኘው አገልግሎት ጋር ካልተመጣጠነ የቀዘቀዘች አገር ውስጥ ነው የሚኖረው፡፡ ህዝብ ደሞዙ ከሚኖረው ኑሮ ጋር ካልተመጣጠነለት ኖረ አይባልም፡፡ ህዝብ ከዕለት ዕለት ህይወት እየከበደው ከሄደ ከሳቁ ምሬቱ፣ ከደስታው ሐዘኑ እየበረታ ሥርዓቱን፣ አገዛዙን፣ ገዢዎቹን፣ አስተዳዳሪዎቹን ይጠላል፡፡ ሀገሩም የእሱ አትመስለውም፡፡ ህዝብ መሰረታዊ የፍጆታ ዕቃዎችን ለማግኘት ነግ-ሠርክ የሚሰለፍ ከሆነ፤ አልፎ ተርፎም ከናካቴው ዕጥረት የሚከሰትበት ሁኔታ ከመጣ፣ ብሶቱ ወሰን አይኖረውም፡፡ ህዝብ በመኖሪያ ቤት ችግር የሚሰቃይ ከሆነ መሰረታዊ የኑሮ አስፈላጊ ነገር ጎሎበታል ማለት ነው፡፡ ከዚህ ሁሉ የሚከፋው ደግሞ ይህንን የሚገልፅበት መንገድ ካጣና በፍርሃት ተሸማቆ ከተቀመጠ ነው፡፡ “አዲስ ያይጥ - ወጥመድ በሰራህ ቁጥር” አዲስ አይጥ የምትወለድ ከሆነ፣ ወይ ወጥመዷ ላይ ወይ አጥማጁ ላይ ችግር አለ ማለት ነው” ይባላል፡፡ በሙስና የተሞላ ልማት ዘርዛራ ወንፊት ነው፡፡ ዕብቁንም፤ እንክርዳዱንም፤ እያሳለፈ፤ እያዩ እህል አለን እንደሚሉት አይነት የዋህነት ይሆናል፡፡ የዚህ ሁሉ መጨረሻው ድህነት ነው፡፡ ድህነት ሲመጣ ቃላት ይበዛል። ስብሰባ፣ ንግግር፣ የማይተገበር ቃል - መግባት እንደህይወት ይወሰዳል፡፡ እንደኑሮ ይለመዳል፡፡ “አንድ መንግሥት ከሌላ መንግሥት የሚማረው ጥበብ ከህዝብ ኪስ ገንዘብ አሟጥጦ መውሰድ ነው” ይለናል፤ አዳም ስሚዝ የጥንቱ የጠዋቱ የኢኮኖሚ ሊቅ፡፡  
አንድ የአሜሪካኖች አባባል አለ:- “በአንድ አገር ከዋናው ይልቅ ምክትሉ ነው ምርጥ ሥራ አለው የሚባለው፡፡ ምክንያቱም ትልቁ ሥራው ጠዋት ሲነሳ ‘ዋናው አለቃ ደህና አደሩ?’ ማለት ብቻ ነው!” ከዚህ ይሰውረን፡፡
ኑሮ እጅግ በከፋ ሁኔታ ላይ ሲገኝ፤ እንግሊዞች “ሶስት ትውልድ ሙሉ ሸሚዛችንን እንደጠቀለልን አለን” ይላሉ፡፡ ጣሊያኖች ደግሞ፤ “ከከዋክብት እስከ ጋጣ/በረት እየኖርን ነው” ይላሉ፡፡ ስፔይኖችም፤ “ሀብትን፤ የሌለው ይሠራዋል። ያለው ያላግባብ ይጫወትበታል” ይላሉ፡፡ ኢትዮጵያውያን፤ “ኑ እስኪለን መከራችንን እናያለን” ይላሉ፡፡ አምላክ አንደኛውን እስከሚጠራን ቀን ድረስ አበሳ ፍዳችንን እየቆጠርን ነው እንደማለት ነው!! ሁሉ የምሬት ቋንቋ አለው! ጊዜውና ደረጃው ይለያይ እንጂ ምሬቱ የሚፈታበትም መንገድ እንደዚያው ይለያያል፡፡ ማናቸውም ዕቅድና ስትራቴጂ ህዝብ ኑሮ ላይ ያነጣጠረ መሆን አለበት፡፡ ይሄ ማለት የእርስ በርስ ሙግትና የአዕምሮ አክሮባት ከመሥራት ይልቅ፤ የህዝቡስ ሁኔታ እንዴት ነው? ማለት ዋና ጉዳይ ነው፣ ማለት ነው፡፡ ለህዝብ ተብሎ፣ በህዝብ ስም የተቀረፀውንም አጀንዳ ለግል ጥቅም እንዳይውል ጠንክሮ መጠበቅ ይገባል፡፡
በሀገራችን “ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል” የተባለው ተረት ዕድሜው እጅግ ረጅም ነው፡፡ የሥርዓቶቻችንን ያህል አርጅቷል፡፡ በተግባር ሲተረጐም ግን ገና ዛሬ የተወለደ ነው የሚመስለው፡፡ በየቢሮው፣ በየማህበሩ፣ በየፓርቲው የምናየው ሀቅ ነው፡፡ “አዲስ እረኛ ከብት አያስተኛ”፣ “እከክልኝ ልከክልህም” አብሮ ሲተረት የኖረ ነው፡፡ እዚህ ላይ፤ ሁለት የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ሲቀያየሩ ሂያጁ ለመጪው ያለውን መጥቀስ መልካም አርአያነት ያለው ነው:-
“እኔ ይሄን ሥልጣን (ቢሮ) ለቅቄ ስወጣና ወደቤቴ ስሄድ፤ የተደሰትኩትን ያህል አንተ ወደዚህ ሥልጣን በመምጣትህ የምትደሰት ከሆነ፤ በዚች አገር የመጨረሻው ከፍተኛ ደስተኛ ሰው አንተ ነህ ማለት ነው!” (ይህን የተባሉት አብርሃም ሊንከን ናቸው) ይሄ መታደል ነው፡፡ በማናቸውም መንገድ ሥልጣን ላይ የሚወጣ ሰው፤ “ሥልጣን በሸተተው ማግስት አካሄዱ ሁሉ ይለዋወጣል፤ እንደድመት ኮርማ ይሆናል” ይባላል፡፡ ከዚህም ይሰውረን። አክብሮታችን ለመንበሩ እንጂ ለሰውዬው አይደለም፡፡ ዞሮ ዞሮ ህዝብን ማገልገያ መንበር መሆን አለበት፡፡ አንዱ ባለሥልጣን ሌላውን ባለሥልጣን የጐዳ መስሎት በሚሠነዝረው ጥቃት የዝቅተኛው ክፍል ህዝብ መጠቃቱ ትልቅ ጉዳት ነው፡፡ አፍ በሰፋ ቁጥር ተሳዳቢው ህዝብ ነው፡፡ የሚላክበት ህዝብ ነው፡፡ ጎረቤትም ቢቆስል ጦሱ ላገር ነው፡፡ የቆሰለ አውሬ ለያዥ ለገራዥ አስቸጋሪ ነው፡፡ ጣጣው ግን የህዝብ ነው፡፡   
ለዚህ ነው “ጅቡን የወጋኸው ምኑን ነው?” ቢሉት፤
“አፉን” አለ፡፡ “አፉን ከወጋኸውማ አሰፋኸው” የሚለው የጉራጊኛ ተረት ለማንም የማስጠንቀቂያ ደውል የሚሆነው!! \\\

Published in ርዕሰ አንቀፅ
Page 3 of 17