ሬስቶራንቶችን በክትፎ፣ ቁርጥና ጥብስ ያወዳድራል
አዋሽ ወይን ፋብሪካ ዘመናዊና ጥንታዊ የአጠማመቅ ዘዴዎችን በመጠቀም “ገበታ” የተሰኘ አዲስና ልዩ የወይን ጠጅ ምርት ለፋሲካ በዓል ማቅረቡን አስታወቀ፡፡
“ገበታ” የሚል ስያሜ የተሰጠው አዲሱ የአዋሽ ምርት ቀይና ነጭ ዘመናይ ወይኖች እንዳሉት ታውቋል፡፡ በሌላ በኩል የከተማዋ ሬስቶራንቶች በምርጥ ክትፎ፣ ቁርጥና ጥብስ ብቃታቸውን የሚያሳዩበት “የአዲስ ምርጥ ሥጋ ውድድር” ማዘጋጀቱን አዋሽ ወይን ለአዲስ አድማስ በላከው መግለጫ ጠቁሟል፡፡
በውድድሩ፤ የአዋሽ አዲስ ምርትን ለማስተዋወቅ እንደሚጠቀምበትም ጠቅሶ ሬስቶራንቶች በክትፎ፣ በቁርጥ፣ በጥብስ ወይም በአንዱ አሊያም በሁለቱም መወዳደር ይችላሉ ተብሏል፡፡
ውድድሩ፣ ደንበኞች በስልክ መልዕክት በሚያደርጉት ምርጫ (ክትፎ፣ ቁርጥ፣ ጥብስ) የሚወሰን ሲሆን ሬስቶራንቶች የመጀመሪያዎቹ 100 ውስጥ ከገቡ በየሳምንቱ እንደሚገለፅላቸው ታውቋል፡፡ ውድድሩ ከሚያዝያ 5-25 ድረስ ለሦስት ሳምንት የሚካሄድ ሲሆን በሶስተኛው ሳምንት መጨረሻ ላይ 50ዎቹ ውስጥ የገቡ ሬስቶራንቶች አዲስ አበባ ውስጥ ከሚገኙት ክትፎ፣ ቁርጥና ጥብስ አቅራቢ ሬስቶራንቶች ውስጥ በደንበኞች የተመረጡና ምርጥ መሆናቸውን የሚያሳይ ልዩ ሽልማት ይቀበላሉ ተብሏል፡፡ በእያንዳዱ ውድድር ከ1-5 የሚወጡ ሬስቶራንቶች አዋሽ በሚሰጣቸው ነፃ ወይን ጠጅ የቅምሻ ዝግጅት እንደሚያካሂዱ ተገልጿል፡፡  

    “በ1ኛው ዙር ጓደኛዬ ስትመዘገብ የሚጠቅም ስላልመሰለኝ፣ ‹መዝግበው ምን ሊያደርጉን እንዳሰቡ ታውቂያለሽ? ከዚህ የከፋ  ነገርስ ቢያጋጥመንስ? ምኑንም ሳታውቂ ዝም ብለሽ ትመዘገቢያለሽ?› በማለት አከላክለናት፡፡ እሷ ግን ‹የትም ቢወስዱኝ ከጎዳና ሕይወት አይከፋብኝም እሄዳለሁ› ስትል ተከራከረች፡፡ ‹ይቅርብሽ፤ ድረሱልኝ ብለሽ ብትጮሂ ማንም የማይሰማሽ አፋር በረሃ ወስደው ነው የሚያጉሩሽ አሉ፡፡ የእኛን ሐሳብ ብትሰሚ ይሻላል፡፡ ….› እያልን ለማሳመን ብንሞክርም እንቢ ብላ ሄደች፡፡
“እኛም ሰቆቃዋን ለመስማት ስንደውልላት፣ ‹ምንም ችግር የለም፤ እናንተ እንዳሰባችሁት አይደለም ሁሉም ነገር ጥሩ ነው፡፡ የፈራነው የውሃውን ችግር ነበር፣ እሱም አለ፡፡ ምግቡ፣ ሕክምናው፣ መኝታው፣ ሥልጠናው… ጥሩ ነው። ትንሽ ያስቸገረን ሙቀቱ ነው፡፡ ቀንና ሌሊት የለውም። ላብሽ ይንዠቀዠቃል። እሱንም ቢሆን ሻወር ስላለ ለቅለቅ ስንል ለጊዜውም ቢሆን እፎይ እንላለን። አካባቢውን ስንለማመድ ደግሞ ይተወናል።› ትለን ነበር፡፡ ‹ስትሄድ ስላከላከልናት ነው እንዲህ የምትለው፤ እኛ የእሷን ፀባይ መች አጣነው? ካሁኑ ሙቀት ምናምን ማለት ጀምራለች። ምን አለፋችሁ፣ በቅርብ ቀን ጥላ ትመጣለች› ብለን ስንጠብቅ ወራት ተቆጠሩ፡፡ ትንሽ ቆይታ ‹በአውቶሞቲቭ ሙያ ልመረቅ ነው› አለችን፡፡
እውነቱን ስንረዳ ግን እሷ ሳትሆን እኛ ነበርን ስህተተኞቹ፡፡ አሁን እሷ በአንድ ድርጅት ተቀጥራ በሙያዋ እየሰራችና ጥሩ ደመወዝ እየተከፈላት ነው፡፡ ‹ምነው ያኔ አብሬአት ተመዝግቤ ቢሆን ኖሮ› በማለት ቁጭት ገባኝና በ2ኛው ዙር ለመመዝገብ ወሰንኩ” ብላለች ከሐረር ከአካባቢ የመጣችው የ19 ዓመቷ ወጣትና በዚህ ሳምንት በአፋር ክልል በአሚባራ ወረዳ ከተቋቋመው አዲስ ራዕይ ማሰልጠኛ ማዕከል በ2ኛ ዙር በልብስ ስፌት (ጋርመንት) ሙያ የተመረቀችው ራሄል፡፡
ራሔል እናትና አባቷን በሞት ስለተነጠቀች ዘመድ ቤት ነበር ያደገችው፡፡ ወደ ታዳጊነት ዕድሜ ስትጠጋና ፍላጎቷ ሲጨምር ያደገችበት የዘመድ ቤት ሊመቻት አልቻለም፡፡ በየጊዜው ጭቅጭቅና ንትርክ ሆነ፡፡ መስማማት ስላቃታት ከቤት ወጥታ ለ5 ዓመት የጎዳና ሕይወት አሳለፈች፡፡ “የጎዳና ህይወት አይመችም፡፡ በተለይ ለሴት ልጅ በጣም አስቀያሚና አሰቃቂ ነው፡፡ መደብደብ፣ ተገዶ መደፈር፣ ህልውና ማጣት፣ ረሃብ፣ ሱሰኛ መሆን፣… በርካታ ችግሮች አሉበት፡፡ ከዚህ መጥፎ ህይወት ቢሻል ብዬ መስተንግዶ ጀመርኩ፡፡ ሁለቱም አንድ ናቸው - የሲኦል ኑሮ” በማለት በምሬት ገልጻለች፡፡
በተለያዩ ምክንያቶች ለልመናና ለጎዳና ህይወት የተጋለጡ ዜጎች በጣም በርካታ ናቸው። እነዚህ ዜጎች የአገሪቷ ሀብት ተቋዳሽ አልሆኑም፤ በጉልበትና እውቀታቸው የልማቷ ተሳታፊ መሆንም አልቻሉም። ይህን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር ለመፍታት መንግሥት የተለያዩ ዘዴዎችን ቀይሶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ይናገራል፡፡
የ2ኛው ዙር ምረቃ የክብር እንግዳና ከፍተኛ ውጤት ላመጡት ሰልጣኞች ሜዳሊያ የሰጡት የአዲስ አበባ ከንቲባ ድሪባ ኩማ ባደረጉት ንግግር፤ የከተማው መስተዳድር ከ2003 እስከ 2005 60 ሚሊዮን ብር መድቦ፣ በአራት ዙሮች 10ሺህ ያህል የጎዳና ተዳዳሪዎች ወደመጡበት ቀዬ መመለሱን፣ አሰልጥኖ በአነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ያደራጃቸው ሰዎች ከ30 ሚሊዮን በላይ መቆጠባቸውን ገልጸዋል።
ይሁን እንጂ መንግሥት ይህን ስር ሰድዶ የቆየውን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግር በቅንጅት ካልሆነ በስተቀር ብቻውን መወጣት አይችልም የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ ለዚህም የሚያቀርቡት ማስረጃ፣ መንግሥት በቅርብ ዓመት በአዲስ አበባ ከተማ በልመናና በጎዳና ተዳዳሪነት ተሰማርተው የነበሩትን ዜጎች አሰልጥኖ መቋቋሚያ ሰጥቶ ወደቀያቸው ቢመልስም ጥለው ተመልሰው በለመዱት ሥራ ተሰማርተዋል ይላሉ፡፡
መንግሥትም ይህን ችግር ለመቅረፍ ከሌሎች አካላት ጋር ተቀናጅቶ መሥራት በመጀመሩ ባለፈው ዓመት መጨረሻ አካባቢ ከብረታ ብረትና ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽንና ከኤልሻዳይ ሪሊፍ ኤንድ ዴቨሎፕመንት አሶሴሽን ጋር በመሆን ባቋቋመው አዲስ ራዕይ ማሰልጠኛ ማዕከል፣ 3,600 የ1ኛ ዙር ሰልጣኞች ማስመረቁን ከንቲባው ተናግረዋል፡፡
የ2ኛው ዙር ሰልጣኞች 4130 መሆናቸውን የጠቀሱት የማዕከሉ አዛዥ ኮሎኔል ገብሩ ገ/ጻድቅ፤ ሰልጣኞቹ በቆይታቸው የኮንስትራክሽን ማሽነሪ ኦፕሬሽንና ጥገና፣ የፋብሪኬሽን (የብረታብረት)፣ የጨርቃጨርቅ (ጋርመንት)፣ የኦቶሞቲቭ፣ የእርሻ መሳሪያዎችና ማሽኒንግ ሙያ በንድፈ ሐሳብና በተግባር መከታተላቸውን፣ 4003 ወንዶችና 136 ሴቶች የሙያ ብቃት ማረጋገጫ ፈተና (COC) ወስደው 4130 ሰልጣኞች በከፍተኛ ብቃት ማለፋቸውን ገልጸዋል፡፡
ከተመራቂዎቹ መካል 1,777 በስኳር ኮርፖሬሽን፣ 1,068 በብረታ በረትና ኢንጂነሪንግ፣ እንዲሁም 240 በአዲስ አበባ መስተዳድር በተለያዩ ቢሮዎች በሾፌርነት መመደባቸውን ጠቅሰው፤ 1,045 ቀጣሪ እስኪያገኙ ድረስ ብረታ ብረትና ኮርፖሬሽንና ኤልሻዳይ አሶሴሽን አስፈላጊ ድጋፍ እያደረጉላቸው በብረታ ብረት ኮርፖሬሽን የተለያዩ ኢንዱስትሪዎች ተመድበው ይቆያሉ ብለዋል፡፡
ብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ኮርፖሬሽን የአጠቃላይ የካምፕ ግንባታና የፋሲሊቲ አቅርቦት፣ አመራር፣ አሰልጣኞችና ድጋፍ ሰጪ ሰራተኞች መመደቡን፣ ለስልጠናው የሚያስፈልጉ ማሽነሪዎችና ሌሎች ቁሳቁሶች ማቅረቡን እንዲሁም ለማሽነሪዎቹ የነዳጅ አቅርቦትና ጥገና ማድረጉን፣ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አንድ አምቡላንስና አንድ ፒክ አፕ መኪና መስጠቱን፣ የብቃት ማረጋገጫ ፈተና የሚሰጡ ባለሙያዎችን ማሰልጠኑንና የፈተናውን አጠቃላይ ወጪ መሸፈኑን፣ ኤልሻዳይ ሪሊፍ ኤንድ ዴቨሎፕመንት አሶሴሽን ደግሞ የምግብ የአልባሳትና የጤና አገልግሎት ወጪ መሸፈኑን አዛዡ አስረድተዋል፡፡
አምና ጠቅላይ ሚ/ር ኃይለማርያም ደሳለኝ በመጀመሪያው ዙር ምረቃ፤ “ይህ ሥራ ሥልጠናና ሥራ ማስያዝ ብቻ ሳይሆን የተረሰና የተዘነጉ ወገኖችን የመለወጥ፣ መንፈስ የማንቃት፣ አመለካከትን የመቀየር ከባድ ሥራ መሆኑ፣ ወገኖቻችንን ቀስቅሶ የልማቱ ተጠቃሚም ጠቃሚም የማድረግ ትልቅ ትዕግስት ይጠይቃል” ማለታቸውን የጠቀሱት የግብርና ዴኤታ አቶ ምትኩ ካሳ፤ ለዚህ ስራ ሁሉም በኃላፊነትም ይሁን በዜግነት ወይም በሰው ልጅነቱ ብቻ ያለ ቀስቃሽ ያገባኛል፣ ይመለከተኛል በማለት ሊረባረብ ይገባል ሲሉ አሳስበዋል፡፡   
ልመናና የጎዳና ተዳዳሪነት ከአገራችን ባህልና ታሪክ፣ ከህዝባችን ጨዋነት፣ ከሞራልና ከሥነ-ምግባር፣ ከእምነትና ማኅበራዊ እሴቶች አንፃር ሲታይ አስነዋሪ ድርጊት የመሆኑ ጉዳይ ክርክር እንደማያስነሳ የጠቀሱት የሰራተኛና ማህበራዊ ሚኒስትር አቶ አብዱልፈታህ አብዱላሂ፤ ልመናና የጎዳና ተዳዳሪነት ሠርቶ የመኖር ፀጋን እየሸረሸረ፣ ተመፅዋችነትና ጥገኝነት እንዲስፋፋ፣ የመልካም አገራዊ እሴቶች ገፅታ እንዲበላሽ አፍራሽ ሚና ይጫወታል ብለዋል፡፡

Tuesday, 14 April 2015 08:31

ሰሙነ ሕማማትና ምስጢሩ

     ከትንሣኤ በፊት ያለው ሳምንት ሰሙነ ሕማማት ይባላል፡፡ ይኸውም በነቢዩ ኢሳይያስ፤ “ነስአ ደዌነ ወፆረ ሕማምነ፤” በእውነት ደዌአችንን ተቀበለ፤ ሕማማችንም ተሸከመ፤ በእርሱ ቁስል እኛ ተፈወስን። (ኢሳ.5፤34-36) ተብሎ በመንፈስ ቅዱስ ትንቢት የተነገረው ቃል ተፈጸመ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ሳምንት ውስጥ ለድኅነት ዓለም ሲል በአጭር ቁመት፣ በጠባብ ደረት ተወስኖ የተቀበለውን ጸዋትወ መከራ ለማስታወስ የወጣ ስያሜ ነው፡፡  
በሰሙነ ሕማማት መስቀል መሳለምና እርስ በእርስ መሳሳም የለም፡፡ ይህም ይሁዳ ጌታን በመሳም አሳልፎ እንደሰጠው ለማሰብ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ውስጥ ያሉት ዕለታት ስያሜያቸውና በየእያንዳንዳቸው ዕለታት የተፈፀሙትን ድርጊቶች እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡
ሰኞ፡- አንጽሖተ ቤተ መቅደስና መርገመ በለስ የተፈፀመበት ዕለት ነው፡፡ የሆሣዕና ዕለት ቢታንያ ያድራል፡፡ በማግስቱም ከቢታንያ ሲመጣ ተራበ “ወበሳኒታ ወፂኦ እምቢታንያ ርኅበ ወርእየ በለሰ እምርሑቅ ወባቲ ቁጽለ ወሖረ ይርአይ እመቦ ዘይረክብ ፍሬ በውስቴታ ፀበጺሖ ኅቤሃ አልቦ ዘረከበ ዘእንበለ ቁጽል ባሕቲቱ እስውመ ኢኮነ ጊዜሁ ለበለስ” ቅጠል ያላት በለስ ከሩቅ ዓይቶ ወደ በለሲቱ ቀረበ፤ ነገር ግን ከቅጠል በቀር አንዳችም ፍሬ አላገኘባትም፤ “ወአውሥኦ ወይቤላ ለዓለም አልቦ ዘይበልዕ ፍሬ እምኔኪ እንከ” ከአሁን ጀምሮ ማንም ከአንቺ ፍሬ አይብላ ብሎ ረግማት፡፡ (ማር. 11፤11-12)
በለስ የተባለች ቤተ እስራኤል ናት፡፡ ፍሬ የተባለች ሃይማኖት ምግባር ናት፡፡ ከእስራኤል ፍቅርን ሃይማኖትን ምግባርን ፈለገ አላገኘም፡፡ እስራኤል ሕዝበ እስራኤል መባል እንጂ ደግ ሰው አይገኝብሽ ብሎ ረገማት፡፡ በመርገም ምክንያት እርሱ ከላያቸው በስተቀር ደግ ሰው ጠፋባት፡፡
አንድም በለስ ኦሪት ናት፡፡ በዚህ ዓለም ሰፍና ቢያገኛት ኦሪትና ነቢያትን ልሽር አልመጣሁም ልፈጽም እንጂ በማለት ፈጸማት፡፡ ሕገ ኦሪትን ከመፈፀም በእሷ ድኅነት አላደረገባትምና ፍሬ በአንቺ አይሁን አላት፡፡ ድኅነት በአንቺ አይደረግብሽ ብሏታልና እንደ መድረቅ አለች፡፡
አንድም በለስ ኃጢአት ናት፡፡ የበለስ ቅጠል ሠፊ እንደሆነች ኃጢአትም በዚህ ዓለም ስፍራ ሰፍና አገኛት፡፡ በለስ ሲበሉት ይጣፍጣል፤ ቆይቶ ግን ይመራል፡፡ ኃጢአትም ሲሠሩት ደስ ያሰኛል፡፡ ኋላ ግን ያሳዝናል፡፡ ወደ እርሷ ሄደ ማለትም ከኃጥአን ጋር ዋለ፤ ኃጥአ ከመባል በቀር በመዋዕሉ ኃጢአት አለመሥራቱን ለመመልከት ፍሬ አላገኘባትም አለ። በአንቺ ፍሬ አይገኝ የሚለውም በኃጢአት በፍዳ ተይዞ የሚቀር  አይኑር ለማለት ነው፡፡ ስትረገም ፈጥና መድረቋም በአዳም በደል ያገኛትን እዳ በደል በእርሱ እንደጠፋችልን ለመግለጽ ነው፡፡
በመቀጠልም ወደ ቤተ መቅደስ ሄደ፡፡ ቤተ መቅደስ ቤተ ጸሎት፣ ቤተ መሥዋዕት መሆኑ ቀርቶ ቤተ ምሲያጥ (የንግድ ቤት) ሆኖ ቢያገኘው “ቤትየሰ ቤተ ጸሎት፣ ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች።
እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችኋት” ብሎ የሚሸጡበትን ሁሉ ገለበጠባቸው፤ ገርፎም አስወጣቸው፡፡ /ማር 11፤17-19/ ይህም የሚያሳየው ማደሪያ ቤቱ የነበርን የአዳም ልጆች ኃጢአት ሰፍኖብን ስንኖር ቢያገኘን፣ ኃጢአታችንን ሁሉ እንዳራቀልን ነው፡፡
በሰሙነ ሕማማት ካህናትና ምእመናን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ወዛቸው ጠብ እስኪል ድረስ በነግህ፣ በሠለስት፣ በስድስት ሰዓትና በተሰዓቱ ሰዓት መላልሰው ሲሰግዱና ሲፀልዩ ይሰነብታሉ፡፡ በተለይም ካህናት በማንኛውም አገልግሎት ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ፡፡ ምክንያቱም የደረሰበትን መከራ፣ ኅዘኑንና 5500 ዘመን የሰው ልጅ በጨለማ ሕይወት ይኖር እንደነበር ለማዘከር ነው፡፡
ማክሰኞ፡- የጥያቄ ቀን በመባል ይታወቃል፡፡ ምክንያቱም ሹመትን ወይም ሥልጣንን ለሰው ልጅ የሰጠ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ሰኞ ባደረገው አንጽሖተ ቤተ መቅደስ ምክንያት በዚህ ዕለት ስለ ሥልጣኑ በጸሐፍት ፈሪሳውያን ተጠይቋልና፡፡
ጥያቄውም “ከምድራውያን ነገሥታት፣ ከሌዋውያን ካህናት ያይደለህ ትምህርት ማስተማር፣ ተአምራት ማድረግ፣ ገበያ መፍታት በማን ሥልጣን ታደርጋለህ?” የሚል ነበር፡፡ “ይህንስ ሥልጣን እነዚህን እንዳደርግ እነግራችኋለሁ፡፡ የዮሐንስ ጥምቀት ከወዴት ነበረች? ከሰማይ ወይስ ከሰው?” አላቸው፡፡ እነርሱም ከሰማይ ነው ብንል ለምን አልተቀበላችሁትም? ይለናል፡፡ ከሰው ነው ብንል ሕዝቡ ሁሉ ዮሐንስን እንደ አባት ያከብሩታል፤ እንደ መምህርነቱም ይፈሩታልና ሕዝቡን እንፈራለን ተባብለው “ወዴት እንደሆነ አናውቅም” ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም “በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ እኔም አልነገራችሁም” አላቸው፡፡ ይህንንም መጠየቃቸው እርሱ የሚያደርጋቸውን ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተውት አልነበረም። ልቡናቸው በክፋትና በጥርጣሬ ስለተሞላ ነው እንጂ። ከዚህ የምንማረው የእነሱን ክፉ ጠባይና ግብር መከተል እንደማይገባን ነው፡፡ በዚህ ዕለት በቤተ መቅደስም ረጅም ትምህርት ስላስተማረ የትምህርት ቀንም ይባላል፡፡ ይኸውም ከሃይማኖት የራቁትን፤ ከፍቅረ እግዚአብሔር የተለዩትን አስተምሮ ማቅረብ፣ መክሮ መመለስ እንደሚገባ ሲያስተምር ነው፡፡
ረቡዕ፡- ይህ ዕለት የምክር ቀን ይባላል፡፡ ምክንያቱም የአይሁድ ሊቃነ ካህትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንደሚገባቸው ምክር የጀመሩበት ወይም የያዙበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡ በዚህ ምክራቸው ላይ በጣም ትልቅ ጭንቀት ነበር፡፡ ምክንያቱም ወቅቱ የፋሲካ በዓላቸውን የሚያከብሩበት በመሆኑ፣ ብዙው ሕዝብም በጌታችን ትምህርት የተማረኩ፣ ተአምራቱን የሚያደንቁ ስለነበር ሁከት እንዳይፈጥር ነው፡፡ በዚህ ጭንቀት ሳሉ ከደቀመዛሙርቱ አንዱ የአስቆሮቱ ይሁዳ በመካከላቸው በመገኘት የምክራቸው ተባባሪ ሆኖ ጭንቀታቸውን አስወግዶላቸዋል፡፡ /ማቴ.26፤1-5፣ ማር.14፤1-2/
የሐዲስ ኪዳን ካህናት ምእመናን በዚህ ዕለት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተሰብስበው ከእህልና ውኃ ተለይተው፣ መላ ሰውነታቸውን ለእግዚአብሔር አስገዝተው፣ የሞት ፍርዱን በማሰብና በማልቀስ፣ ስለዚህ የሚያወሳውንም በማንበብ፣ እስከ ኮከብ መውጫ በጾም፣ በፀሎትና በስግደት ተወስነው ይቆዩና ወደ ቤታቸው ይሄዳሉ፡፡
ይሁዳ ማለት ታማኝ ማለት ቢሆንም እንደስሙ ግብሩ ሆኖ አልተገኘም፡፡ ስምና ግብሩ አልተባበረለትም፡፡ እኛስ እንደ ስማችን ይሆን ግብራችን?
መልካም መዓዛ ያለው ቀንም ይባላል፡፡ ምክንያቱም ጌታችን በዚህ ዕለት በቤተ ስምዖን ዘለምጽ ተቀምጦ ሳለ መላ ሕይወቷን ለዝሙት አስገዝታ ትኖር የነበረችው ማርያም እንተ እፍረት “ከእንግዲህ በኃጢአት ተጐድቶ ይኖረ የነበረውን ሕይወቴን እንደዚሁ መልካም ሽቶ የሚያጣፍጥ፣ ኃጢአትን ይቅር የሚል አምላክ መጣ” ስትል ዋጋው እጅግ በጣም ውድ የሆነ ከሦስት መቶ ዲናር በላይ የሚያወጣ በአልባስጥሮስ ብልቃጥ የሞላ ሽቱ ይዛ በመሄድ በጠጉሩ /በራሱ/ ላይ በማርከፍከፍ ስላቀረበች ነው፡፡
የእንባ ቀንም ይባላል፡፡ ይህም ይህችው ሴት በጌታችን እግር ላይ ተደፍታ መላ ኃጢአቷን ይቅር እንዲላት በእንባዋ እግሩን አጥባዋለችና፡፡ /ማቴ.26፤6-13፣ ማር.14፤3-9፣ዮሐ.12፤1/ ከዚህም እያንዳንዳችን ልንማር የሚገባን ነገር አለ፡፡ ይኸውም የራስን ኃጢአት በማሰብ ማልቀስና የተወደደ መሥዋዕት አድርጐ ለእግዚአብሔር ማቅረብን ነው። ሐሙስ፡- ከስቅለትና ከትንሣኤ በፊት ያለው ሐሙስ በቤተክርስቲያናችን የተለያዩ ስያሜዎች አሉት፡፡
ሕጽበተ እግር ይባላል፡፡ ይህ ስያሜ የተሰጠው ጌታችን በዚህ ዕለት የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠቡ ምክንያት ነው፡፡ ይህም የሚያሳየው የዓለምን ኃጢአት ለማጠብ የመጣ መሆኑን ነው፡፡ ይህንን ለማስታወስ ዛሬ ካህናት በተለይም ሊቃነ ጳጳሳት፤ “በመካከላችን ተገኝተህ የእኛንና የሕዝቡን ኃጢአት እጠብ” ሲሉ በቤተ ክርስቲያናችን የተገኙትን ምእመናን እግር በወይንና በወይራ ቅጠል ሲያጥቡ ያረፍዳሉ፡፡ /ዮሐ.13፤4-15/
የጸሎት ሐሙስ ይባላል፡፡ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ የሚደክም ሥጋን የተዋሐደ አምላክ ፍጹም ሰው መሆኑን ለመግለጽና ለአርአያነት ጠላቶቹ መጥተው እስኪይዙት ድረስ በጌቴ ሴማኒ ሲፀልይ በማደሩ ምክንያት ነው፡፡ /ማቴ.26፤36፣ ዮሐ.17፤1/
የምስጢር ቀንም ይባላል፡፡ ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አንዱ በዚህ ዕለት ተመሥርቷል። ይኸውም “ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው፤ እንካችሁ ብሉ፡፡”ጽዋውንም አንስቶ አመሰገነ “ይህ ስለ እናንተ ነገ በመስቀል የሚፈስ ደሜ ነው፤ ከእርሱም ጠጡ፡፡” በማለት እኛ ከእርሱ ጋር አንድ የምንሆንበትን መንገድ ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመሆኑ የተሰጠ ስያሜ ነው፡፡ በዚህ ዕለት ቅዳሴ ይቀደሳል፡፡ የሚቀደሰውም በለሆሳስ ሲሆን እንደ ቃጭል በመሆን የሚያገለግለውም ጽናጽል ነው፡፡ ይህም አይሁድ ጌታችንን ለመያዝ ሲመጡ ድምጻቸውን ዝግ አድርገው በለሆሳስ እየተነጋገሩ መምጣታቸውን ለማሰብ ነው። በቅዳሴውም ኑዛዜ አይደረግም፡፡ ሥርዓተ ቁርባን ግን ይፈጸምበታል፡፡ ይህም ጌታችን የሰጠውን ዘለዓለማዊ ቃል ኪዳን ለማሰብ ነው፡፡ በዚህ ዕለት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በንስሐ ታጥቦ ተዘጋጅቶ፣ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን መቀበል ይኖርበታል፡፡
የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል፡፡ ምክንያቱም መሥዋዕተ ኦሪት ማለትም በእንስሳ ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ፣ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጐ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ ነው።                 /ሉቃ.22፤18-20/ “ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው ደሜ የሚሆን የአዲስ ኪዳን ነው፡፡ ከእርሱም ጠጡ” በማለቱ ይታወቃል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ዘለዓለማዊ ቃል ኪዳን በራሱ ደም የፈጸመበት ዕለት መሆኑን በማሰብ፣ የቃል ኪዳኑ ፈጻሚዎች ጠባቂዎች መሆን እንደሚገባን እንማራለን፡፡
የነጻነት ሐሙስ ይባላል፡፡ ለኃጢአትና ለዲያብሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱ፣ የሰው ልጅ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡ ራሱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለሰው ልጅ ነጻነት ሲናገር፤ “ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም፤ ባሪያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና፤ ወዳጆቼ ግን ብያችኋለሁ” በማለቱ /ዮሐ.15፤15/ ከባርነት ነጻ የወጣንበት ቀን መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ ያስረዳል፡፡ ስለዚህ እያንዳንዱ ክርስቲያን ከኃጢአት ባርነት በመራቅ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያወዳጀውን መልካም ሥራ በመሥራት፣ ሕይወቱን በቅድስና መምራት ይኖርበታል፡፡ እርሱ ጠላቶቹ ስንሆን ወዳጆቹ አድርጐናል፡፡ /ማቴ 24፤17-19/
6. አረንጓዴው ሐሙስም ይባላል፡፡ ይህም ጌታችን
  መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአትክልት ቦታ
   ስለጸለየ ነው፡፡
ዕለተ ዓርብ፡- /የስቅለት ቀን/ ስቅለት፣ መስቀል፣ መሰቀል፣ አሰቃቀል ማለት ነው፡፡ መስቀል በቁሙ መስቀያ፣ መመዘኛ፣ መሰቀያ፣ መንጠልጠያ፣ ለሞት የሚያበቃ መከራ፡፡ በማር 8፤34፤ “ወደውፆሙ ለሕዝብ ምስለ አርዳኢሁ ወይቤሎሙ ዘይፈቅድ ይፀመደኒ ይድልአ ለነፍሱ ወያጥብዕ ወይፀር መስቀል ሞቱ ወይትልወኒ” ከደቀ መዛሙርቱም ጋር ሕዝቡን ጠርቶ እንዲህ አላቸው፤ “ሊከተለኝ የሚወድ ሰው ራሱን ይካድ፤ ጨክኖም የሞቱን መስቀል ተሸክሞ ይከተለኝ” ይላል፡፡
ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በ1ኛ ቆሮ፣ 1፡17 ላይ፤ “ወኢኮነ በጥበበ ነገር ከመ ኢንሰዐር መስቀሎ ለክርስቶስ” የክርስቶስን መስቀሉን ከንቱ እንዳናደርግ ነገርን በማራቀቅ አይደለም… ይላል፡፡
ጌታችን በተሰቀለ ዕለት ከስድስት ሰዓት ጀምሮ እስከ ዘጠኝ ሰዓት ድረስ በምድር ሁሉ ላይ ጨለማ ሆነ፡፡ /ፀሐይ ጨለመ/፣ እነሆም የቤተ መቅደስ መጋረጃ ከላይ እስከ ታች ከሁለት ተቀደደ፤ ምድርም ተናወጠች፤ ዓለቶችም ተሰነጠቁ፤ መቃብሮችም ተከፈቱ፤ ተኝተውም ከነበሩት ቅዱሳን ብዙ ሥራዎችን ተነሱ፤ ከትንሳኤውም በኋላ ከመቃብሮች ወጥተው ወደ ቅድስት ከተማ ለብዙዎች ታዩ፡፡ /ማቴ.27፤51/
ጌታችን ለዓለሙ ያሰበውን ቤዛነት ሊፈጽም በመስቀል ላይ መሰቀሉ የሚታሰብበት ነውና ለስቅለቱ መታሰቢያ የሚሆን አጎበር ተዘጋጅቶ፣ ከርቤ እየታጠነ፣ ስቅለቱን የሚመለከቱ ምንባባት በወርድ ሲነበቡና ሲሰገድ ይዋላል፡፡ የሰው ልጅ በሙሉ በእግረ አጋንንት ረግጦ፣ ከፈጣሪው ተጣልቶ ለ5500 ዘመን በጨለማ መኖሩን ለማስታወስም መንበሩ ታቦቱ በዚህ ቀን በጥቁር ልበስ ይሸፈናሉ፡፡ /ወያለብሱ ታቦተ ልብሰ ጸሊመ/ ዲያቆኑም በቤተ ክርስቲያን በመዞር የሚያሰማው የቃጭል ድምጽ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለቅሶ፣ አንድም ዋና ዋና እያሉ የተከተሉት የኢየሩሳሌም ሴቶችን መሾም ምሳሌ ነው፡፡ /ሉቃ. 23፡31/
ቀዳም ሹር፡- የስቅለት ማግስት የሚውለው ቅዳሜ ወፍጮ ስለሚፈጭበትና ሌላም ለፋሲካ የሚኾን ሥራ ስለሚሰራበት ቅዳሜ ሹር /የተሻረ ቅዳሜ/ ተባለ፡፡ ምስጢሩ ግን ክርስቲያኖች በዘመነ ሐዲስ በቅዳሜ ፈንታ እሑድን ማክበራቸውን ያሳያል፡፡ ይኸውም የተጀመረው በታላቁ ቆስጠንጢኖስ ዘመን ነው፡፡
ቀዳም ሥዑር በጾም፡- የተሻረ ጾም ውሎ የሚያድርበት የአክፍሎት ቀን ማለት ነው። /መዝ. 88፤44/ “ወሠዐርኮ እምንጽሑ፣ ከንጽሕናውም ሻርከው እንዲል ቅዱስ ዳዊት”
ቅዳም ሥዑር፡- የለመለመ ዕለት ቄጤማና ግጫ የሚታደልበት /መዝ. 22፡2  “ውስተ ብሔር ሥዑር ሕየ የኅድረኒ፣ በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፡፡ ቄጤማ በረግረግ ቦታ ላይ የሚበቅል ለምለም ሣር ነው፡፡ “በውኑ ደንገል ረግረግ በሌለበት መሬት ይበቅላልን? ወይስ ቄጤማ ውኃ በሌለበት ቦታ ይለመልማል?” /ኢዮብ 8፡11/ ግጫ እንግጫ የእንቁጣጣሽ ሣር ወይም በበዓል ጊዜ ቤት ውስት የሚጎዘጎዝ፡፡ /ኢሳ.19፡5/
በዕለተ ዓርብ ነፍሳት ከሲኦል ወጡ፡፡ አንቀጸ ገነት ተከፈተልን፣ ርስተ መንግስተ ሰማያት ተመለሰችልን፤ አባታችን አዳምም ከፈጣሪው ጋር ታረቀልን በማለት “ገብረ ሰላመ በመስቀሉ ትንሳኤሁ አግሃዶ” እያልን የተድላ፣ የደስታ ምልክት ወይም መገለጫ የሆነ ልምላሜ ያለውን ቆጽለ ሆሣዕና ወይም ቄጤማ ግጫ ይዘን የምስራች እንባባላለን፡፡ /ኤፌ.2፡14-15/ “ወዘእንበለ ምሳሌሰ ኢተናግሮሙ፣ ያለ ምሳሌ አልተናገረምና እንዳለ /ማቴ 13፡34-35/ በኖኅ ጊዜም ርግብ “ሐጸ ማየ አይኅ፣ ይትባ ማየ አይኅ፣ የጥፋት ውኃ ጎደለ፣ አለቀ እያለች     ቆጽላ ዕፀ ዘይት ይዛ ለኖኅ አብስራዋለች፡፡ /ዘፍ. 8፡8-11/
ርግብ የካህናት፣ ኖኅ የምእመናን፣ ኖኅ እጁን ዘርግቶ ርግብን እንደተቀበላት ካህናትም በየመንደሩ እየዞሩ “ክርስቶስ ተመረመረ፤ ዲያብሎስ ታሰረ” በማለት ቄጤማ ሲያድሉ፤ ምእመናንም እጃቸውን ዘርግተው መቀበላቸው የዚህ ምሳሌ ነው፡፡
ስለዚህ አሁንም ቢገኝ የወይራ ልምላሜ ቢታጣ ግጫን እየታደልን የምሥራች መባባላችን ነፍሳት ከሲኦል ለመውጣታቸው መታሰቢያ ነው፡፡ ይህን ቆጽላ ልምላሜ ይዞ ተድላ፣ ደስታ መግለጽ ከጥንት ጀምሮ ሲያያዝ የመጣ ነው እንጂ እንግዳ ነገር አይደለም፡፡ ለዚህ በመጀመሪያዪቱ ቀን ከበጎ እንጨት ፍሬን፣ የሰሌንና የተምር ዛፍ ልምላሜ ይዛችሁ በየዓመቱ ሰባት ቀን ተድላ፣ ደስታ ታደርጋለችሁ ብሏል፡፡ /ዘሌ. 23፡40-44/
በሰሙነ ሕማማት ጊዜ ቤተ ክርስቲያናችን የምታደርገው ትውፊት የሐዋ. ሥራ 1፤3
ከሆሣዕና እስከ ቅዳም ሥዑር ያሉት ዕለታት የዓመተ ፍዳ መታሰቢያ ናቸው፡፡ የሆሣዕና ዕለት ካህናት ቅዳሴ ከምዕራብ ወደ ምስራቅ መግባታቸው ከአዳም ጀምሮ እስከ ስቅለት ያሉ ነፍሳት ወደ ሲኦል መውረዳቸው አምሳል ነው፡፡ ጸሎተ ፍትሐት አይደረግም፡፡ በዚህ ሳምንት ውስጥ ለሚሞቱ ምእመናን እግዚኦ ሕያዋን ይደገማልና፡፡ በሰሙነ ሕማማት መስቀል የለም። ሳምንቱ የዘመነ ኦሪት ምሳሌ ስለሆነ እርስ በእርስ በመሳሳም፣ ሰላም መባባልና መልክዐ መድገም የለም። ይኸውም ይሁዳ ክርስቶስን በሰላምታ ስላስያዘው እርሱን ላለመምሰል፡፡ /ማቴ. 26/
በዚህ ሳምንት ብሉያትና ሐዲሳት መጻሕፍት ከጥዋት እስከ ማታ ይነበባሉ፡፡ የአምልኮ ስግደት ይሰገዳል፡፡ ይኸውም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ ሲል መስቀልን ተሸክሞ ሲወድቅ ሲነሣ የዋለበትን፣ ይልቁንም ሥርዓተ ስግደትን ራሱ ሰግዶ እኛን ያስተማረንን በማሰብ ነው፡፡ /ሉቃ. 22፡41-45፣ ዩሐ፣ 4፡22-24/
ስለዚህም በዚህ ሣምንት ወርኃዊ፣ ዓመታዊ በዓል ቢሆን እንኳ ስግደት አይቋረጥም፡፡ የአምልኮ ስግደት ሳምንት ስለሆነ፡፡ ዲያቆኑ ጥቁር ለብሶ መስቀል ይዞ ቃጭል እያቃጨለ ቤተ ክርስቲያንን ሦስት ጊዜ መዞሩ፣ ዲያቆኑ በዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ፣ ቃጭል የእመቤታችን ምሳሌ ሲሆኑ፤ ዮሐንስና እመቤታችን ጌታችን የተሰቀለበትን እግረ መስቀሉን እየዞሩ አልቅሰው ነበርና፡፡
በዕለተ ዓርብ ሰርክ ሲሆን ምእመናን ወደ ቄሱ እየቀረቡ ስግደት እንዲሰጣቸው ይጠይቃሉ፡፡ ቄሱም በወይራ ቅጠል እየጠበጠበ ተጨማሪ ቀን ሲሰግዱ ከዋሉት ሌላ ስግደት ይሰጣቸዋል፡፡ ጥብጣብ የጌታችን ግርፋት ምሳሌ ነው፡፡ አንድም  የተግሣፅ ምሳሌ ነው፡፡ /ማቴ. 26፡27/
አክፍሎት
አክፈለ፣ አካፈለ፣ ደረበ እያሳገሩ መብላትን ግብረ ሕማማትም ያዛል፡፡ አክፍሎት ማለት ማካፈል፣ ማጠፍ፣ መደረብ፣ ሁለቱን ቀን አንድ ቀን አድርጎ መጾም፣ ጌታ ከተያዘበት እስከተነሳበት ድረስ ይህ ሥርዓት የመጣው በቤተ ክርስቲያናችን ልማድ እመቤታችን፣ ያዕቆብና ዮሐንስ የጌታን ትንሳኤ ሳናይ እህልና ውኃ አንቀምስም ብለው እስከ ትንሳኤ በመቆየታቸው ምክንያት ነው። በሀገራችን ብዙ ሰዎች ሐሙስ ማታ የቀመሱ እሁድ የትንሳኤ ዕለት ብቻ እህልና ውኃ የሚቀምሱ ሲሆን ያልተቻላቸው ግን ዓርብ ማታ ትንሽ ቀምሰው እስከ ትንሳኤ ይሰነብታሉ፡፡ የሁለቱ ቀን ማክፈሉ እንኳ ቢከብድ ቅዳሜን ማክፈል ሥርዓት ነው፡፡ ቅዳሴው በመንፈቀ ሌሊት ስለሆነ በልቶ ማስቀደስና መቁረብ እንዳይሆን፡፡

Published in ህብረተሰብ

     ሰሞኑን የወጣውን የዳንኤል ክብረት “እኛ የመጨረሻዎቹ እና ሌሎች” የተሰኘ መጽሐፍ አንብቤ ስጨርስ ነው ይህን ጽሑፍ ለመፃፍ የተነሳሁት፡፡ በዚህ መፅሐፍ ውስጥ የተለያዩ ወጐች ተካትተዋል። ከነዚህ ወጐች መካከልም በገፅ 133 የሚገኘው “እስከ ሰባት ትውልድ” የሚለው ይገኝበታል፡፡
ዳንኤል ክብረት በሌሎች መጽሐፍቱ የምናውቀው ትልቅ ደራሲ ነው፡፡ “እኛ የመጨረሻዎቹ እና ሌሎች” በተባለው አዲሱ መጽሐፍ ውስጥ ያገኘሁት የታሪክ ግድፈት ግን ከትልቅ ደራሲ የማይጠበቅ ትልቅ ስህተት ሆኖብኛል፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ በርካታ የታሪክ ግድፈቶች ቢኖሩም በዚህ ጽሑፍ ግን በጣም ጐልቶ የታየውን አንዱን ብቻ እነግራችኋለሁ፡፡
“እስከ ሰባት ትውልድ” የሚለው ወግ አጠቃላይ ጭብጡ መጪውን ዘመን አስበን ካልሰራን የትውልድ መበላሸት እንደሚፈጠር የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ለዚህ ጭብጥ ደራሲው የተለያዩ አጫጭር ታሪኮችን በመጥቀስ መልእክቱን ሲያጠናክር እናስተውላለን፡፡ ለምሳሌ በመስቀሉ ጦርነት ወቅት አውሮፓውያንን አሸንፎ እየሩሳሌምን ስለተቆጣጠረው ሳላሐዲን ይናገራል፡፡ ዳንኤል ክብረት እንደሚለው፤ ሳላሐዲን እየሩሳሌምን ከተቆጣጠረ በኋላ የክርስቶስን መቃብር ለማየት ወደ ጐለጐታ ይሄዳል፡፡ በጐለጐታ የነበሩ ቄሶች ሳላሐዲንን እያስጐበኙት ሳለ የስግደት ሰዓት ደረሰበት፡፡ ሳላሐዲንም ጉብኝቱን አቋርጦ ወጣ። በወቅቱ የነበሩት መነኮሳት እዚያው እንዲሰግድ ቢነግሩትም ሳላሐዲን ግን፤ “እኔ የሰገድኩበትን ቦታ መጪው የሙስሊም ትውልድ ሊነጥቃችሁ ይችላል” በማለት ከጐለጐታ ወጣ ብሎ ሰገደ። ሳላሐዲን ያለው አልቀረም፤ ያ ቦታ በኋላ ዘመን መስጊድ ተሰራበት፡፡ ሳላሐዲን በጐለጐታ ቢሰግድ ኖሮ በክርስቲያኖች እና በሙስሊሞች መካከል ጊዜ ጠብቆ የሚፈነዳ ቦንብ ይኖር ነበር… በማለት ዳንኤል ክብረት በመጽሐፉ አውግቶናል፡፡
ውድ አንባቢያን ሆይ፤ እኔን የገረመኝ በክርስትናም ሆነ በእስልምና ሃይማኖት ውስጥ የክርስቶስ መቃብር የሚባል አለመኖሩ እየታወቀ ደራሲው ግን ይህንን ማስፈሩ ነው፡፡ እንደ ክርስትና እምነት ከሆነ፣ የክርስቶስ አካል ያረፈበት ዋሻ ነበር። ከሶስት ቀን በኋላ ግን ክርስቶስ ተነስቶ ማረጉን ሐይማኖቱ ይነግረናል፡፡ ዳንኤል ክብረት ይህን ማለት ፈልጐ ከሆነ በግልጽ ማስቀመጥ ነበረበት፡፡ ሁለተኛ ነገር ደግሞ ሳላሐዲን ሙስሊም መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ በእስልምና አስተምህሮት ደግሞ ክርስቶስ ከነህይወቱ አርጓል የሚል እንጂ ተቀብሯል የሚል እምነት የለም፡፡ አይሁዶች እየሱስን ለመግደል ወይም ለመያዝ ወደ እርሱ ዘንድ ሲሄዱ፣ አምላክ እየሱስን ወደ እርሱ ዘንድ እንዲያርግ አድርጐታል ነው የሚለው እስልምና። ታዲያ ክርስቶስ አልተቀበረም ብሎ የሚያምነው ሳላሐዲን፤ የቱን መቃብር ነው የጐበኘው? የትኛው ታሪክ ውስጥ ነው የክርስቶስን መቃብር ለማየት ሳላሐዲን ወደ ጐለጐታ መጣ ተብሎ የተፃፈው?
ውድ አንባቢያን ሆይ፤ እኔ በዋናነት ለማንሳት የፈለግሁት ይህን አይደለም፡፡ ዳንኤል ክብረት ያነሳው ይህ ታሪክ የሳላሐዲን አልነበረም፡፡ ትልቁ ስህተትም እዚህ ላይ ነው፡፡ ይህ ታሪክ በ638 ዓመት የተፈፀመ የካሊፍ ኡመር ታሪክ ነው፡፡ ሳላሐዲን በ11ኛው ክ/ዘመን የኖረ የጦር ሜዳ ጀግና ሲሆን ኡመር ደግሞ በ6ኛው ክ/ዘመን የነበረ የሙስሊሞች ሁለተኛው ካሊፍ (ንጉስ) ነው፡፡
ከነብዩ ሙሐመድ ሞት በኋላ ከአቡበከር ቀጥሎ የንግስናውን መንበር የጨበጠው ኡመር ነበር። እስልምና በርካታ ግዛቶቹን ያስፋፋው በኡመር ዘመነ መንግስት ነው፡፡ እየሩሳሌምም በሙስሊሞች እጅ የወደቀችው በዚሁ ዘመን ነበር፡፡ እየሩሳሌምን ከሌሎች ግዛቶች የሚለያት ምንም ደም ሳይፈስ የኢስላም ግዛት አካል ለመሆን መቻሏ ነው፡፡
ግዛቶችን እያስፋፋ የመጣው የሙስሊሞች ጦር፣ ወደ እየሩሳሌም ሲገሰግስ ባዛንታይኖች ሶሪያን ለመልቀቅ ተገደዱ፡፡ በኡመር ኢብን አል አስ የሚመራው የሙስሊሙ ጦር ሰተት ብሎ እየሩሳሌም ገባ፡፡ በወቅቱ የእየሩሳሌም ፓትሪያርክ ሶፍሮኒያስ ነበር፡፡ ቄስ ሶፍሮኒያስ በካቶሊክ እና በምስራቅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ዘንድ እንደ ቅዱስ የሚታይ ሰው ነው፡፡ ሶፍሮኒያስ የሙስሊሞቹን ጦር መቋቋም እንደማይችል በተገነዘበ ወቅት ህዝቡን ከእልቂት ለመታደግ እየሩሳሌምን ለኡመር አገዛዝ ለማስረከብ ወሰነ፡፡ ይህን ለማድረግ የጠየቀው ቅድመ ሁኔታ ግን ነበር፤ ንጉስ ኡመር እየሩሳሌም ድረስ መምጣት አለበት የሚል፡፡ የከተማዋን ቁልፍ የሚያስረክበው ለማንም ሳይሆን ለንጉስ ኡመር ብቻ መሆኑን አሳወቀ፡፡
ይህ መልዕክት የደረሰው ከሊፋ ኡመር አጠገቡ የነበሩትን ሰዎች ካማከረ በኋላ ከመዲና (ሳኡዲ አረቢያ) ተነስቶ ወደ እየሩሳሌም ተጓዘ፡፡ ከሊፋ (ንጉስ) ኡመር እየሩሳሌም በፈረስ እንደገባ አቀባበል ተደረገለት፡፡ በዲንጋ ቆሽሸው የነበሩ የቤተ - መቅደሶቹን አካባቢ ልብሱን ተጠቅሞ አፀዳቸው። (በወቅቱ አይሁዶች ቤተ መቅደሱ ዘንድ እንዳይገቡ በመከልከላቸው ሮማውያኖች ቦታውን በቅጡ አልያዙትም ነበር)፡፡ የኡመርን ተግባር የተመለከቱት የሙስሊሞቹ ጦር ልክ እንደሱ አደረጉ፡፡ ከዚያም እየሩሳሌምን መጐብኘት ጀመረ፡፡ ከሊፋ ኡመር ቤተ - መቅደሶቹን እና ቤተ - ክርስቲያናትን በመጐብኘት ላይ ሳለ የሶላት (ስግደት) ሰዓት ደረሰበት፡፡ ኡመርን የሚያስጐበኙት ቄሶች እዚያው እንዲሰግድ ቢነግሩትም ኡመር ግን እንቢ አለ፡፡ “እኔ እዚህ ከሰገድኩኝ መጪዎቹ የሙስሊም ትውልዶች ኡመር የሰገደበት በሚል ቦታውን ይነጥቋችኋል።” በማለት ከቤተ - ክርስቲያኑ ራቅ ብሎ ሰገደ፡፡ ኡመር ያለው አልቀረም፤ እርሱ በሰገደበት ቦታ ላይ በኋላ የመጡ የሙስሊም ትውልዶች መስጊድ ገነቡበት፡፡ ይህ መስጊድ አሁን ድረስ በእየሩሳሌም ውስጥ የሚገኝ ሲሆን “ኡመር መስጂድ” በመባል ይጠራል፡፡
እየሩሳሌም በሰላማዊ መንገድ በሙስሊም አገዛዝ ስር ከወደቀች በኋላ ንጉስ ኡመርና ቄስ ሶፍሮኒያስ ስምምነት አደረጉ፡፡ ምንም አይነት ግድያ እንደማይፈፀም፣ የክርስቲያኖች ንብረት እና የፀሎት ቦታ እንደማይነካ፣ ማንኛውም የክርስትና አማኝ እምነቱን በነፃነት የማራመድ መብት እንዳለው እና ሌሎችንም ስምምነቶች ኡመር በፊርማው ለሶፍሮኒያስ አረጋገጠለት፡፡
በወቅቱ አይሁዶች ወደ እየሩሳሌም እና ቤተ - መቅደሶቹ ዘንድ እንዳይገቡ በሮማውያን ተከልክለው ነበር፡፡ ይህ ህግ እንዲከበር ሶፍሮኒያስ ጠየቀ፡፡ ንጉስ ኡመር የሶፍሮኒያስን ጥያቄ የተቀበለ ቢሆንም በኋለኛው የሙስሊሞች ዘመን ግን አይሁዶች መግባት ተፈቅዶላቸዋል፡፡
በአጠቃላይ በእስልምና አገዛዝ ስር ክርስቲያኖችም መብት እንዳላቸው ኡመር ካረጋገጠላቸው በኋላ ወደ መዲና (ሳኡዲ አረቢያ) ተመለሰ፡፡ ያን ዘመን ተከትሎ ነበር እየሩሳሌም የሶስቱ ታላላቅ ሐይማኖት ተከታዮች የጋራ መኖሪያ የሆነችው፡፡ ለእስልምና፣ ክርስትና እና ለአይሁድ እምነቶች፡፡
ከላይ የገለፅነው የኡመር ተግባር በሐይማኖት ውስጥ መቻቻል እና አብሮ መኖር ሲወሳ፣ እንደ ተምሳሌት ተደርጐ አብሮ ይጠቀሳል፡፡ ይህ ታሪክ “Jerusalem is ours: The Centuries old Christian, Islam and Struggle for Holy Land”  በተባለው መጽሐፍ ውስጥ ሰፍሮ ይገኛል። በሌሎች የኢንተርኔት ፅሁፎች ውስጥም በብዛት አለ፡፡ ውድ አንባቢያን ሆይ፤ በዳንኤል ክብረት ወግ ውስጥ ሳላሐዲን በሚል የቀረበው ታሪክ የእርሱ ሳይሆን የንጉስ ኡመር ታሪክ ነው፡፡ ትልቅ ስህተት - ከትልቅ ደራሲ ይሏችኋል ይህ ነው፡፡ ሰላም!!

Published in ህብረተሰብ
Tuesday, 14 April 2015 08:28

የትንሳኤ ስጦታ

ክርስቶስ ሊረሳን አይችልም፤ በእጆቹ መዳፍ ላይ ተቀርፀናል፡፡
ሌይስ ፒቺሎ
በምንም ዓይነት አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ብሆን የክርስቶስ ትንሳኤ ለህይወቴ ትርጉምና አቅጣጫ እንዲሁም እንደ  አዲስ የመጀመር ዕድል ይሰጠዋል፡፡
ሮበርት ፍላት
እኛ ኖረን እንሞታለን፤ ክርስቶስ ሞቶ ይኖራል፡፡
ጆን ስቶት
ሰዎችን ከጊዜ ቅንብብ ውስጥ አውጥቶ ዘላለማዊነት እንዲሰማቸው ያደርጋል፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኢመርሰን
የእኔ አምላክ ከዚህ ምድር፣ ከዚህ መቃብር፣ ከዚህ አቧራ ውስጥ እንደሚያወጣኝ አምናለሁ፡፡
ዋልተር ራሊግ
ትንሳኤ፤ እግዚአብሔር ህይወት መንፈሳዊና ዘላለማዊ መሆኑን ማሳያው ነው፡፡
ቻርልስ ኤም ክሮው
ትንሳኤ እንዲህ ይለናል፡- “እውነትን ልትቀብራት ትችላለህ፤ ግን ተቀብራ አትቀርም”
ክላረንስ ደብሊው ሆል
የክርስቶስን ስቅለት ባሰብኩ ቁጥር የቅናት ኃጢአትን እፈፅማለሁ፡፡
ሳይሞን ዌይል
ክርስቲያን ማለት በሁሉ ነገር ከክርስቶስ ጋር የሚጓዝ አይደለም፡፡ እንዲህ ያለው ብቃት ማናችንም ጋ የለም፡፡ ክርስቲያን ማለት ትክክለኛውን መንገድ ያገኘ ነው፡፡
ቻርልስ ኤል. አለን
የኢየሱስ ክርስቶስ ደም እጅግ አያሌ ሃጢአቶችን የሚከላከል ይመስለኛል፡፡
ዴኒስ ዲድሮት
እንደ ኢየሱስ ማንም ወዶ አያውቅም፡፡ ዓይነስውርን አብርቷል፤ ዲዳን አናግሯል፡፡ እኛን ለማዳን በመስቀል ላይ ተቸንክሯል፡፡ አሁን እግዚአብሔር፤ “እሱ ይሄን በማድረጉ ምሬአችኋለሁ” ብሎናል፡፡
ቢሊ ግራሃም
ኢየሱስ የመጀመሪያው ሶሻሊስት ነው፤ ለሰው ልጅ ሁሉ የተሻለ ህይወት ለመፍጠር የተጋ የመጀመሪያው ሰው፡፡
ሚኻኤል ጎርባቾቭ

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
እንኳን ለብርሀነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁ!
ቀለልና ዘና ያለ፣ በሦስተኛው ቀን የማያነጫንጭና ከራስና ከሌሎች ጋር የማያጣላ በዓል ይሁንልንማ! ኑሮን የማያስጠላ የበዓል ሰሞን ያድርግልንማ!
የምር ግን በዓል ስንቀበል እንዴት እንደሆነ ልብ ብላችሁልኛል? በቃ ምን አለፋችሁ…ድፍን አገር በቁመትም ይሁን በክብደት ቅደም ተከተል ተሰልፎ “ኪስህን ክፈት…” እየተባለ ገንዘብ የተጠቀጠቀለት ነው የሚመስለው፡፡ የዝንቦች ‘ዳንሲንግ ዊዝ ዘ ስታርስ’ ምናምን አይነት ውድድር ሲካሄድበት የነበረው ሱቅ ሁሉ ግፊያ ይሆናል፡፡ እነሱ እኛን እንደሚሉን እኛም እነሱን… “እኔ የምለው ሰዉ ከየት ነው ገንዘብ የሚያመጣው?” እያልን እንተዛዘባለን፡፡ በዛ ሰሞን፣ ገንዘብ ከመቸገሩ የተነሳ… “እኔ የምፈራው ይህች ዓለም የበቃችኝ ዕለት ገመድ እንኳን መግዣ እንዳላጣ ነው…” አይነት ነገር ሊል ጫፍ የደረሰው ሁሉ የበዓል ሰሞን ባለ‘ሳይንቲስቱን’ እያከታታለ ሲመዠርጠው…አለ አይደል… የምትናገሩት ይጠፋችኋል፡፡
በዓልን በጨፈገገ ፊት ከማክበር ያድነንማ!
ስሙኝማ…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… ለበዓል እኮ ቆፍረንም፣ ቧጠንም ቢሆን ‘የልምዳችን አትቀርም፡፡’ ሰዋችን የቆጠባትንም ቢሆን አውጥቶ ‘ከሰው እኩል’ ይሆናታል እንጂ የጎረቤትን የሽንኩርት ቁሌት እያሸተቱ ማን በሩን ዘግቶ ይውላል! ነገርዬው… አለ አይደል… “የማን ቤት ሞቆ የማን ይበርዳል!” አይነት ነው፡፡
ስሙኝማ...በዓላት ሰሞን ኤ.ቲ.ኤሞች አካባቢ ያለውን ግፊያ ልብ ብላችኋል! እናማ…ሰዋችን ሀኪም “ገዝተህ ተጠቀም…” ያለውን አሞክሲሊን ምናምን ለመግዛት ሰባ ሰማንያ ብር ለማውጣት ሲያቅማማ ቆይቶ በዓል ሲሆን ግን ያውም ተጋፍቶ ሺህ ምናምኑን ያወጣል…ያን ያህል ከቀረ ማለት ነው፡፡
ነገርዬው የሚመጣው ከጥቂት ቀናት በኋላ የበዓሉን ሰሞን ስንሸኝ ነው፡፡ ያኔ ጠብ ከቤት ይጀመራል፡፡
“እ! ታዲያ እኔ ሽንኩርት ሆኜ ድስት ውስጥ ልገባልህ ነው!…”
“እና ከየት ላምጣልሽ! የለገደምቢ የወርቅ ማዕድን የእሱ ነው አሉሽ እንዴ!” ምናምን አይነት ‘እሰጥ አገባ’ ይጀመራል፡፡
“አሁን ይሄ ወር እንዴት ሊገፋ ነው!
“አንድ ሊትር ዘይት እንዲህ ይረርብን!”
“አሁን ይሄ ኑሮ ነው…ሦስት ኪሎ ሽንኩርት ለመግዛት ሠላሳ ምናምን ብር ቤቱ ውስጥ ይጥፋ!” ምናምን ይባላል፡፡ (ስሙኝማ…‘እንደ አካሄዷ’ ከሆነ ሽንኩርትም እንደ ‘ዳይመንድ’ ዲታ ሆድ ውስጥ ብቻ ልትገኝ ነው፡፡ ልክ ነዋ… ይልቁንም የምግብ ባለሙያዎቻችን ከ‘ሽንኩርት ነጻ’ የሆነ ሹሮ እንዴት እንደምንሠራ የሆነ ዘዴ ይፍጠሩልንማ…የሹሮ እህልም እንደ ለገደንቢ ወርቅ ሩቅ እስኪሆንብን ድረስ ማለት ነው! (ስለኑሮ መወደድና ‘ፍሬኑ ስለተበጠሰው’ የዋጋ ነገር አገር አቀፍ ኮንፍረንስ ይጠራልንማ፡፡)
እናላችሁ… ስንቀበለው “ሆዴ፣ አንጀቴ…” ያልነውን ነገር ሁሉ ስንሰናበተው “ዓይንህ ለአፈር…” አይነት ነገር ማለት እየለመድነው መጣን መሰለኝ። ቀድሞውኑም ‘የመጀመሪያ ፍቅራችን’ ጣራ ይነካል፤ በኋላም ‘የመጨረሻ ጥላቻችን’ እንዲሁ ጣራ ይነካል። ምን አለፋችሁ… ተመስገኖ መጥቶ ተመስግኖ የሚመለስ ነገር እየጠፋ ነው፡፡
‘ፍቅር ሲጠና ቆሎ ያጓርሳል’ የሚሏት ነገር አለች።
ስሙኝማ… ለምሳሌ ለመጀመሪያ ጊዜ አዲስ እንትናዬ ስትገኝ ያለው ውዳሴ… አለ አይደል… “እንዲች አይነት ቆንጆና ንጹህ ልብ ያላት ሴት ልብ ወለድ ውስጥስ ትገኛለች!” ያሰኛል፡፡  
“የእኔ ጌታ መልኳ በል፣ ጠባዩዋ በል… እንዴት አድርጎ ቢፈጥራት ነው የምታሰኝ ነች፡፡”
ፍቅር ሲጠና ቆሎ ያጓርስ የለ!
ሲጣሉ ደግሞ ምን ይባላል መሰላችሁ… “ብታያት እኮ የሆነች አስጠሊታ፡፡ መልክ የላት፣ ጠባይ የላት… ስጡላ ሰው ይሉሀል እሷ ነች፡፡ ጭራና ቀንድ የሌላት ሰይጣን በላት፡፡”
ያጓረሰ ፍቅር ሲያልቅ ደግሞ ያናክሳል፡፡
ደግሞላችሁ…መሥሪያ ቤት አዲሰ አለቃ ይመጣል፡፡ ገና ከዋዜማው ‘በእሳቸው መጀን’ አይነት ነገር ይጀመራል፡፡
“መሥሪያ ቤታችን ሊያልፍለት ነው፡፡”
“መሥሪያ ቤታችን በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የተዋጣለት ሥራ አስኪያጅ ሊመጣለት ነው…”
“የእንትን ፋብሪካ ሠራኞች ሲወዱት!”
“ሊለቅ እንደሆነ ሲሰሙ ሲላቀሱ ነው የዋሉት አሉ፡፡”
እናላችሁ…ሦስት ወር እንደቆየ… አለ አይደል…ያጓረሰ ፍቅር ማናከስ ይጀምራል፡፡
“ሰውየው ጨረሰን እኮ! ማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ያልጻፈው ለራሱ ብቻ ነው፡፡”
“ለሚያወራው እንኳን ለከት የሌለው! እኔ የምለው ይሄ አይነት ‹ቦካሳ› ምናምን ከየት ነው ያመጡት!”
“አልሰማችሁም… ቢሮ ውስጥ እኮ ነው እንትን የሚለው! ከመሥሪያ ቤቱ ሴቶች የቀረችው አበሩ ነች አሉ፡፡ እሷም የዓመት ፈቃድ ስለወጣች ስላላገኛት ነው!” (ቂ…ቂ…ቂ…)
አዲስ የሂሳብ ክፍል ኃላፊ ይመጣል፡፡
“ለክሩ የሚሞት እንዴት ያለ ታማኝ ሰው መሰላችሁ፡፡ የበፊተኛው እኮ የድርጅቱን ገንዘብ በጠጅ ነው የጨረሰው አሉ፡፡”
“እንኳን የሌላ ሰው ገንዘብ ሊመኝ የራሱን ገንዘብ አውጥቶ ነው የሚሰጠው…” ምናምን እየተባለ ይወራል፡፡
ትንሽ ወራት ቆይቶ ያጓረሰ ፍቅረ ማናከስ ይጀምራል፡፡
“ባንክ እኮ ምንም ገንዘብ አልተረፈም ነው የሚባለው…”
“ቀምቃሚ  ነው አሉ፣ ገንዘባችንን ሁሉ በጠጅ ጨረሰው እኮ…”
“መጀመሪያውኑ እኮ እሱን ገንዘብ ያዥ ይሁን ያለው ማነው! የታወቀ ሞላጫ አይደል እንዴ…” “የሚኖርበት ሰፈር ሴቱን ሁሉ ቅምጥ አስቀምጦ ባለ አበባ ቀሚስና አምበሬ ጭቃ እየገዛ ሲያድል ነው የሚውለው አሉ…” ምናምን ይባላል፡፡
የምር ግን…ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…የአምበሬ ጭቃ ዘመን ናፈቀንሳ! አምበሬ ጭቃ ቀላል ‘ወጪ ቆጣቢ’ ነች እንዴ! ‘ጆርጂዮ አርማኒ’ የለ፣ ‘ሁጎ ቦስ’ የለ፡ ‘ሻነል’ ምናምን የለ…አምበሬ ጭቃ የገዛ እንትና እኮ… አለ አይደል… ለቄሶች ቢነገርለት ስሙ ቅዳሴ ውስጥ ይገባ ነበር!  
እናላችሁ…ያጓረሰ ፍቅር ማናከስ ሲጀምር እንዲህ ነው፡፡
እሷና እሱ ቆሎ ሲጓረሱ ይከርሙና ቸኮላቱ ሁሉ አመድ፣ አመድ ማለት ይጀምራል፡፡ እናማ…እሷዬዋ ምን ትላለች…
“ለአንተ ያለኝ ፍቅር አልቋል፡፡ እንካ ቀለበትህን። ሰለሞንን ነው የምወደው፡፡”
“ሰለሞን የት ነው ያለው?”
“ምን ልታደርግ… ልትጣላ!”
“ነጻ ባወጣኝ ምን አጣላኝ! ይልቅ ቀለበቱን ስንት እንደሚገዛኝ ጠይቂልኝ፡፡”
እናማ አንዳንዴ ፍቅር ሲበቃው ቀለበት ያሸጣል።
ይቺን ስሙኝማ…ሰውየው ለጓደኛው… “ሚስቴን ልፈታ ነው፣” ይለዋል፡፡ ጓደኝየውም፤
“ለምንድነው የምትፈታት? ትወዳት አልነበር እንዴ!” ሲል ይጠይቃል፡፡
“ተለውጣለች፣ ይኸው አራት ወር ሙሉ አላነሰገረችኝም፣” ይላል፡፡ ጓደኝየው ምን ቢለው ጥሩ ነው፡
“ታዲያ እንዲህ የመሰለች የተባረከች ሚስት ነው የምትፈታው! የእኔዋ እኮ አይደለም በአራት ወር በአራት ቀን የሁለት ዓመቱን ነው የምታወራው…”
ቆሎ ያጓረሰ ፍቅር ሲያናክስ አሪፍ አይደለም፡፡
በዚህ በበዓላት ሰሞን ሁሉም ነገር በልክ ይሁንማ!
በድጋሚ እንኳን ለብርሀነ ትንሳኤው በሰላም አደረሳችሁ!
ደህና ሰንብቱልኝማ!


Published in ባህል

--አሁን የወነጨፉት ቀስት ጲላጦስ በጭራሽ ሊቋቋመው የሚችለው አይነት አይደለም፡፡ አይሁድ ይህንን ያውቃሉ፡፡ ጉዳዩን ፖለቲካ አደረጉት፡፡ ሊያውም የስልጣን፡፡… ጲላጦስ፣ ኢየሩሳሌምን ያስተዳድር ዘንድ የተሾመው በሮማው ቄሳር ነው፡፡ እናም የሿሚውን ክብርና ጥቅም ሊያስጠብቅ ግድ አለበት፡፡--  

     እነሆ ዛሬ የትንሣኤ በዓል ዋዜማ “ቀዳም ስዑር” ነው፡፡ ቀዳም ስዑርን “ቅዳም ሹር” ይለዋል ሀገሬው- ከራሱ ዘዬ ጋር አልምዶና አዋህዶ፡፡ ሊባኖንን “ሊባኖስ”፣ አሪስቶትልን “አሪስጣጣሊስ”፣ ፕሌቶንን “አፍላጦን” እንደሚለው፡፡ “ነገርን ነገር ይጠራዋል” እንዲሉ፣ ዕለቱን ማሰቡ ያልኩትን አስባለኝ እንጂ ነገሬስ ከዛሬ 2000 ዓመታት በፊት ትናንት አስበነው በዋልነው ዕለተ አርብ ጠዋት፣ በኢየሩሳሌም ከተማ በጲላጦስ ችሎት ስለሆነውና ስለሁነቱ ሰበብ “መጣፍም የሊቅ አፍም” የሚሉትን ቅጥ አስይዞ ማውሳት ነው፡፡
የዕለተ አርቡን ሁነት ሳስብ የክስተቱ ሰበዝ የሚመስሉኝ ሳይበድል መከራ ተቀበሎ የተሰቀለው ኢየሱስ፣ ወንጀለኛ ሆኖ ሳለ “በለስ ቀንቶት” እና በደሉን የሚወርስለት አግኝቶ ከእስር ነጻ የወጣው በርባን እና በአይሁድ ሤራ ተጠልፎና ለፍርድ ተቸግሮ አብዝቶ የዋለለው ጲላጦስ ናቸው፡፡… ኢየሱስ፣ በርባን፣ ጲላጦስ!
ህዝቡን ሲያስተምር የነበረው ኢየሱስ፤“ህዝቡን አስቶአል! አሳምፆአልም! ንጉሥ ነኝ፤  የእግዚአብሔርም ልጅ ነኝ ብሎአል!”… ብለው የካህናትና የህዝቡ አለቆች ባቀረቡበት ክስ ተይዞ፣ ሌሌቱንም ሙሉ በሹሙ በቀያፋ ግቢ መከራን ሲቀበል አድሮ፣ አርብ ጠዋት የኢየሩሳሌም ገዢ በነበረው በጲላጦስ ችሎት በጲላጦስ ፊት ለፍርድ ቆሞአል፡፡ አብዝተው ቢያንገላቱትም ተቃውሞ፣ ለፌዝና ሹፈታቸውም ምላሽ አልሰጠም። ጥያቄዎቻቸው ተንኮልን እንዳቋቱ ያውቃልና ለመመለስ ብዙም አልተበረታታም፡፡…
በርባን ወንጀለኛ ነው፡፡ ሊያውም ከመንጠቅ ነፍስ እስከማጥፋት የደረሰ፡፡ በዚህም በመላው ኢየሩሳሌም የሚታወቅና እጅጉን የሚፈራ ወንበዴ!... ስለሆነም በእስር ቤት ተጥሎ፣ በጥብቅ እየተጠበቀ ነው፡፡ የበርባን ወንጀል የበዛና የከፋ ነውና ከእስር ነጻ ሊወጣ የሚችልበት አንዳችም ምክንያት የለም። ምናልባትም ወደፊት እስከ ሞት ሊደርስ የሚችል ቅጣት ሊደርስበት ይችላል፡፡ ማንም የሚያውቀው ይህንን ነው፡፡ እውነቱ ይህ ነውና፡፡ የሆነው ግን ሌላ ነው፡፡ ለምን?.... የመሆኑ ጓዝና ሰበብ ብዙ ነው፡፡ እንደሚመስለን የበርባን ነጻ መለቀቅ ህዝቡ “በርባንን ልቀቀው!” በማለት አብዝተው ወደ ጲላጦስ ስለጮሁ ብቻ የሆነ አይደለም፡፡ ሤራ አለው፡፡ ከአጋጣሚና ከእድል ያለፈ ሤራ!
ጲላጦስ፤ ኢየሩሳሌምን ያስተዳድር ዘንድ በሮማዊው ቄሳር የተሾመ የኢየሩሳሌም ገዢ ነው፡፡ በመሆኑም በግዛቱ የሚኖረውን ህዝብ ሊያስተዳድር ብቻ ሳይሆን በተለይም የቄሳሩን ጥቅምና ክብር ሊያስጠብቅ ግዴታና ኃላፊነት አለበት፡፡… ከከተማው ህዝብ ጋር በተለይም ከካህናትና ከህዝቡ አለቆች ጋር ብዙ ቅሬታዎች ቢኖሩትም ተንኮለኞችና ቀናተኞች መሆናቸውን ያውቃልና ሁሌም ጉዳያቸውን የሚያየው በጥንቃቄ ነው፡፡ እነሆ ዛሬም አርብ ማለዳ እነዚሁ የአይሁድ አለቆች፣ ኢየሱስ ላይ ያቀረቡትን ክስ መርምሮ ይፈርድ ዘንድ አፉን እንኳ በቅጡ ሳያብስ ተጣድፎ በችሎቱ ተሰይሞአል፡፡
የካህናትና የህዝቡ አለቆችም ጲላጦስ ኢየሱስ ላይ ሞት ይፈርድበት ዘንድ እጅጉን አሲረውና ተስፋ አድርገው በጉጉት በችሎቱ ፊት ቆመዋል፡፡ ኢየሱስ ሊያሰቅለው የሚችል ጥፋት እንዳልፈጸመ ያውቃሉናም ጲላጦስን አጣብቂኝ ውስጥ ከትተው፣ ኢየሱስ ላይ ሞት ሊያስፈርዱ ሤራን አሲረዋል፡፡ ታላቅ ሤራ!
እንግዲህ የሆነው ሁሉ መሆን የጀመረው እንዲህ ነው፡፡ ከሳሾች፣ ተከሳሽና ዳኛ በችሎቱ ቆመዋል። ከእዚህ ጉዳይ ጋር በምንም ሁኔታ የማይገናኘው ወንጀለኛው በርባንም በእስር ቤት ሆኖ የሚሆነውን እየጠበቀ ነው፡፡… እነሆ የክሱን ሂደት ተከትሎ አይሁድ የቀበሩት ፈንጂ መፈንዳት፣ ያደሩት ሤራ መተርተር፣ የቆፈሩት ጉድጓድም የምር ማጥለቅ… ጀመረ፡፡
በውጤቱ በርባን ነጻ ቢወጣም፣ ኢየሱስ ቢሰቀልም፣ አይሁድ ቢደሰቱም… “ሳይወድ” የዚህ ሁሉ ዋና ተዋናይ የሆነው ግን ጲላጦስ ነው- ቃታውን ባይስብም ለሳቢዎች አሳልፎ የሰጠው!... “ሳይወድ” ያልኩት ከነገሩ አብዝቶ ሊሸሽ በመሞከሩ ነው፡፡ እናም የሆነው ሁሉ የሆነበትን ሰበብና ግፊት እንረዳ ዘንድ ጲላጦስን ይዘን እንቀጥል፡፡
የህዝብ አለቆችና የካህናት አለቆችን ተንኮልና ክፋት የሚያውቀው ጲላጦስ፣ በኢየሱስ ላይ የቀረበውን ክስ በጥንቃቄ መመርመር ይዞአል። ለዚህም ክሱንና ምስክሮቻቸውን በጥሞና አድምጦአል፡፡ ኢየሱስንም ስላንተ በሚሉት ላይ “ምን ትላለህ?” ብሎ ደጋግሞ ጠይቆታል፡፡ እርግጡ ይህ ነው፡፡ ጲላጦስ ብዙ ቢደክምም አንዳችስ እንኳን ወንጀል ኢየሱስ ላይ አላገኘበትም፡፡ ግን ደግሞ በነጻ አለቀቀውም፡፡ ያም ቢቀር ቢያንስ ሰቅለው እንዳይገድሉት ማድረግ አልቻለም፡፡ ደግሞም ቀንተውና ተመቅኝተው እንደከሰሱት ያውቃል፡፡ ስልጣኑ እያለው፣ ሊያድነው እየቻለ ነው የወደዱትን እንዲያደርጉበት አሳልፎ የሰጣቸው፡፡ ለምን?
አንዱ መልስ በእርግጠኝነት “በነቢያት የተነገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ” የሚለው ነው፡፡ እሱን ሳንገፋ በዚያች ቅጽበት የሆነው ሁሉ እንዲሆን ግፊት የነበሩ ጉዳዮችን ማውሳታችንን እንቀጥል፡፡ አሁንም ወደሆነው ሰበብ የሚያደርሰን ጲላጦስ ነውና ከእሱ ጋር ነን፡፡
ጲላጦስ፣ለአርብ አጥቢያ ሌሊቱን እንደ ሁልጊዜው ሁሉ ከሚስቱ ከአብሮቅላ ጋር አድሮ ማልዶ ወጥቶአል፡፡ ሚስቱ ከተኛችበት ስትነቃ ጲላጦስ የለም፡፡ ሌሊቱን በህልሟ ስትሰቃይ አድራለችና ተጨነቀች፡፡ ደግሞም ጲላጦስ የማንን ክስ ለማየት እንደሄደ ታውቃለች፡፡… መልዕክት ላከችለት፡፡ እንዲህ ብላ፤ “በህልሜ አንተን ታላቅ ዘንዶ ሲውጥህ፣ እኔም በእሳት ስገረፍ አይቼአለሁና፣ እዚህ ሰው ላይ ክፉ ነገር እንዳታደርስ፡፡”
እንኳንስ ይህ መልዕክት ተጨምሮለት ኢየሱስ አንዳች እንዳላጠፋ ይልቁንም ከሳሾቹ ተመቅኝተው እንደከሰሱት ጲላጦስ ቢያውቅም ነጻ አላወጣውም። ከሳሾቹንና ያሰለፉትን ህዝብ ፈርቶአል፡፡… እናም በብልሀት ለማለፍ ይልቁንም ከነገሩ ራሱን ለማውጣት ይመስላል ዙሪያ ገባውን ቀዳዳ እየፈለገ ነው፡፡ በዚህ መካከል ታዲያ ከከሳሾቹ አንደበት አንዲት ቃል ወጣች፤ “ከገሊላ ጀምሮ እስከ እዚህ በይሁዳ ሁሉ ያስተምራል” የምትል፡፡
ጲላጦስ፤ “ገሊላ” የምትለውን ቃል ይዞ ማምለጫውን አሰመረ፡፡ የገሊላ ገዢ ሄሮድስ ነው። እናም በወቅቱ በኢየሩሳሌም ይገኝ ወደነበረው ሄሮድስ ኢየሱስን ላከው፡፡ ጲላጦስ ይህን ያደረገው ይህቺን ቀዳዳ በመጠቀም ከነገሩ ለማምለጥ አስልቶ እንጂ ፈልጎና አምኖበት አይደለም፡፡ እንዴት? ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ጲላጦስና ሄሮድስ ጠበኞች ናቸው። የጠባቸውም ምክንያት የግዛት ጥያቄ ነው። በመሆኑም ጲላጦስ ምንም ቢሆን እጁን ለሄሮድስ መስጠት አይፈልግም፡፡… ነገር ግን ሄሮድስ፤ ጲላጦስ የኔን ክብር ተረድቶአል ብሎ በመደሰት ራሱ ጉዳዩን ይዳኛል፤ እኔም ከነገሩ አመልጣለሁ ብሎ ተስፋ አደረገ፡፡ ሆኖም የጲላጦስ ቀመር ሳይሰራ ቀረ፡፡ ሄሮድስ፤ ጲላጦስ ባደረገው ነገር ቢደሰትም ኢየሱስን ጥቂት አንገላቶ ወደ ጲላጦስ መለሰው፡፡
ተስፋው የከዳው ጲላጦስ፤ ከራሱ ጋር ሲመክር ቆይቶ አሁንም ሌላ ማምለጫ መንገድ ፈጠረ፡፡ አቆብቁበው ወደሚጠብቁት ከሳሾች ፊቱን መልሶ፤ “ለፋሲካ በዓል አንድ እስረኛ ልፈታላችሁ ልማድ አለኝና ኢየሱስን ልፍታላችሁ” አላቸው፡፡… ከሳሾቹ ግን ቀላል አይደሉም፡፡ ቀድመው የሸረቡትን ሤራ አንቀሳቀሱት፡፡ ጲላጦስ ይህንን ሊል እንደሚችል ስለገመቱ፣ “ጲላጦስ ይህንን ሲል በርባንን ፍታልን ትላላችሁ” ብለው አሰልፈው ያመጡትን ህዝብ ቀድመው አሳምነዋል፡፡ ስለሆነም ህዝቡ፤ “በርባንን ፍታልን! ኢየሱስን ስቀለው!” አሉ፡፡ በዚህም ጠላታቸውና የሚፈሩት ወንበዴው በርባን ነጻ እንዲሆን አብዝተው ጮሁ፡፡… አንዳንድ ህዝብ እንዲህ ነው፡፡ አጥፊውን ይሻል፡፡
ግን ለምን በርባንን? አንዳንድ መረጃዎች እንደሚነግሩን፣ በርባን ወንበዴ ቢሆንም ከብዙዎቹ የኢየሱስ ከሳሾች ጋር ወዳጅነት ነበረው፡፡ እናም ጥቅማችን ነው የሚሉትን በርባንን ለማስፈታትና ጥቅማችንን ተቃውሞአል ያሉትን ኢየሱስን ለማሰቀል ተጣደፉ፡፡ “በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ!”… ጲላጦስ በርባንን ፈታው፡፡ ሸንጎና ዳኝነት ፍፁም አይደሉም፡፡ እንዲህ በሤራ ይፈታሉ፡፡ ይክሳሉ ሲባሉ እንዲህ ይበድላሉ፡፡ ይኸው ነው፡፡ አለማጥፋት ብቻውን በሸንጎ ፊት ነጻ አያደርግም!
አሁን ጲላጦስ መላወሻ አጥቶአል፡፡ የሞከራቸው ማምለጫዎች ሁሉ እጅጉን ተዘጋጅተው በመጡት የካህናትና የህዝብ አለቆች እየተዘጉ ነው፡፡…  እናም “ኢየሱስን ምን ላድርገው?” የሚለው አቅም የለሽ ጥያቄው በአለቆቹ ተመክሮ ከመጣው ህዝብ፤ “ስቀለው! ስቀለው!” የሚል ምላሽ ተሰጠው፡፡… አንዳች ጥፋት እንዳላገኘበት ደጋግሞ ቢነግራቸውም አልሰሙትም፡፡ ይልቁንም ከሳሾቹ የመጨረሻ የሆነውን የቃላት ቀስታቸውን ወነጨፉ፡፡ እንዲህ ብለው፤ “የእስራኤል ንጉሥ ነኝ ይላል፡፡ ለቄሳርም ግብር አትስጡ ብሎአል፡፡ እኛ ከቄሳር በቀር ሌላ ንጉሥ የለንም፡፡ ካልሰቀልከው አንተ የቄሳር ወዳጅ አይደለህም!…”
አሁን የወነጨፉት ቀስት ጲላጦስ በጭራሽ ሊቋቋመው የሚችለው አይነት አይደለም፡፡ አይሁድ ይህንን ያውቃሉ፡፡ ጉዳዩን ፖለቲካ አደረጉት። ሊያውም የስልጣን፡፡… ጲላጦስ፣ ኢየሩሳሌምን ያስተዳድር ዘንድ የተሾመው በሮማው ቄሳር ነው። እናም የሿሚውን ክብርና ጥቅም ሊያስጠብቅ ግድ አለበት፡፡  እያሉት የነበረውም ይህንን ነው፡፡ ጲላጦስም ነገሩ ስለገባው በሚገባ ተደናገረ፡፡… እናም ተስፋ በመቁረጥ ውስጥ ሆኖ የመጨረሻ ሙከራውን ይፈጽም ዘንድ ተነሳ፡፡ ኢየሱስን አስገረፈው፡፡… ጲላጦስ ኢየሱስን ሲያስገርፍ አሁንም አንድ መውጫን ተስፋ አድርጎአል፡፡ በሕጋቸው የተገረፈ አይሰቀልም፤ የሚሰቀልም አይገረፍም፡፡ እናም ካስገረፍኩት ይተዉታል፣ አይሰቅሉትም… ብሎ አስቦ ነበር፡፡
የኢየሱስ ከሳሾች ግን ይህ አልገታቸውም፡፡ ይልቁንም ሤራቸው በመስራቱ እየተደሰቱ (ከሕግ ውጪ) በሮማ ግዛት ሁሉ ተፈጽሞ የማያውቀውን ሊፈጽሙበት ኢየሱስን እጃቸው አደረጉት፡፡ ይህንን የተረዳውና አቅሙን የጨረሰው ጲላጦስ የማይጠቅምና ያልረባ ነገር አደረገ፤ “እኔ ከዚህ ሰው ደም ንፁህ ነኝ” ብሎ እያልጎመጎመ እጁን ታጠበ፡፡ አቅም ያጣ ገዢ!
ኢየሱስን እያንገላቱ ወስደው በመስቀል ላይ ሰቀሉት፡፡ ጲላጦስ ግን ከዚህ ሁሉ ሽንፈት በኋላ አሁንም ተስፋ የቆረጠ አይመስልም፡፡ ኢየሱስ በተሰቀለበት መስቀል ራስጌ ላይ “ኢ.ና.ን.አ.” (የናዝሬቱ ኢየሱስ የአይሁድ ንጉሥ) የሚል ጽሑፍን አሰቀለ፡፡ የኢየሱስ ሰቃዮች፤ “ለምን እንዲህ ብለህ ትጽፋለህ?” ቢሉትም “የጻፍኩትን ጻፍኩ!” አላቸው፡፡ ጲላጦስ ለምን ይህንን ጻፈ? መልሱን ለማወቅ ቀድሞ ብዙ መጠየቅ ግድ ነው፡፡ ይህንን የመሰሉ ጥያቄዎች፡፡ ጲላጦስ ከዳኝነቱ ለመውጣትና ከነገሩ ለመሸሽ ለምን ፈለገ? ኢየሱስንስ ከመሰቀል ሊያድነው ለምን አብዝቶ ደከመ? ለምን...?
ሚስቱ ህልሟን ስለላከችበት ይሆን? ወይስ የከሳሾቹን ክፋት ያውቅ ስለነበር? ወይንስ ኢየሱስ ላይ ጥፋት ስላላገኘበት?... ያም ሆኖ ልቡ እንደ ብራና በየአቅጣጫው ተወጥራ ሲንገላታና ሲረታ ያረፈደው ጲላጦስ፣ በመጨረሻ የልቡን እምነትና ሀሳብ ኢየሱስ በተሰቀለበት መስቀል ራስጌ ላይ በመስቀል ያሸነፈ ይመስላል፡፡ “ኢ.ና.ን.አ”
መልካም ትንሣኤ!!

Published in ህብረተሰብ

     የዓለም አገራት ፓስፖርቶች ሁሉ ተመሳሳይ ናቸው፡፡ መጠናቸውም ቢሆን 125 ሚሜ x 88 ሚሜ ገደማ ነው፡፡ የየአገራቱ ፓስፖርት አንዱ ከሌላው የሚለየው በምን መሰላችሁ? ያለ ቪዛ ወደ ስንት የዓለም አገራት በቀላሉ ያስገባሉ በሚለው ነው፡፡ ሲሼልስ ዜጎቿ ያለ ቪዛ ውጣ ውረድ በርከት ወዳሉ የዓለም አገራት በቀላሉ እንዲገቡ የሚያስችል አስተማማኝ ፓስፖርት ያላት አፍሪካዊ አገር ናት። የኤርትራ ፓስፖርት ደግሞ የዓለም አገራትን ጉዞ አስቸጋሪ ያደርጋል ተብሏል፡፡
የአፍሪካ አገራት ፓስፖርቶች ያለ ቪዛ ወይም መድረሻ ላይ በሚመታ ቪዛ ወደ ስንት የዓለም አገራት ሊያስገቡ ይችላሉ የሚለውን በመፈተሽ “Good” መፅሄት 7 ቀዳሚ የአፍሪካ አገራትን ለይቶ ደረጃ ሰጥቷቸዋል፡፡ ጥናቱ እንደሚያሳየው፤ የሲሼልስ ፓስፖርት ያላቸው ዜጎች ለቪዛ ማመልከት ሳያስፈልጋቸው 126 አገራትን በነፃነት መጎብኘት ይችላሉ፡፡ ሞሪሽየስና ደቡብ አፍሪካ ደግሞ በሁለተኛና ሦስተኛነት ደረጃ የአፍሪካ አስተማማኝ ፓስፖርቶች ሆነዋል፡፡ የአፍሪካ ግዙፍ ኢኮኖሚ ባለቤት የሆነችው ናይጄሪያ ግን በዚህ ረገድ በ33ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡
በዓለም ደረጃ ፊንላንድ፣ ስዊድንና ዩናይትድ ኪንግደም የዓለማችን የመጀመሪያዎቹ ሶስት አስተማማኝ ፓስፖርቶች ባለቤት ሲሆኑ ዜጎቻቸው ወደ 137 አገራት ያለምንም ውጣውረድ በቀላሉ እንዲገቡ ያስችላሉ፡፡ አፍጋኒስታን ከዓለም የመጨረሻ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡
በዓለም ላይ ቪዛ በከፍተኛ ደረጃ ከሚጠየቅባቸው ክልሎች አንዷ አፍሪካ ስትሆን በአፍሪካ አገራት መካከል ያለው ጥብቅ የቪዛ ቁጥጥር የኢኮኖሚ ዕድገቱን ክፉኛ እንደጎተተው ይነገራል፡፡ ከዚህ በታች “Good” መፅሔት “7ቱ አስተማማኝ የአፍሪካ ፓስፖርቶች” በሚል በደረጃ ያስቀመጣቸውን አገሮች እንመለከታለን፡፡
ሲሼልስ - ለ129 አገሮች ቪዛ አያስፈልግም
የሲሼልስ ዜጎች ወይም ፓስፖርት ባለቤቶች ያለ ቪዛ ወይም መድረሻቸው ላይ በሚመታላቸው ቪዛ ወደ 126 አገራት በቀላሉ መግባት ይችላሉ፡፡ የሲሼልስ ፓስፖርት ዜጎችን ከዓለም አገራት ጋር በቀላሉ በማገናኘት ከአፍሪካ የአንደኝነት ደረጃ ሲይዝ ከዓለም በ28ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡
ሞሪሺየስ - ለ125 አገሮች ቪዛ አያስፈልግም
በአፍሪካ ከሲሼልስ ቀጥሎ ወደ ብዙ የዓለማችን አገራት በነፃነት የሚጓዙት የሞሪሺየስ ዜጎች ናቸው፡፡ የዚህች አገር ፓስፖርት ያለ ቪዛ ወይም መድረሻ ላይ በሚመታ ቪዛ ወደ 123 አገራት ያስገባል፡፡ በዚህም በአፍሪካ 2ኛው አስተማማኝ ፓስፖርት ተብሏል፡፡
ደቡብ አፍሪካ - ለ94 አገሮች ቪዛ አያስፈልግም
ደቡብ አፍሪካውያን ለፓስፖርታቸው ምስጋና ይግባውና ከዓለማችን 194 አገራት ውስጥ ወደ 97 ያህሉ ያለ ቪዛ መግባት ይችላሉ፡፡ የደቡብ አፍሪካ ፓስፖርት ከሲሼልስና ሞሪሽየስ ቀጥሎ በአፍሪካ እጅግ አስተማማኙ ፓስፖርት በመሆን 3ኛ ደረጃን ይዟል፡፡
ቦትስዋና - ለ73 አገሮች ቪዛ አያስፈልግም
የአህጉሪቱ አራተኛው አስተማማኝ ፓስፖርት ያለው በቦትስዋና ዜጎች እጅ ሲሆን ከዓለም በ58ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡ የቦትስዋና ፓስፖርት ወደ 73 አገራት ያለ ቪዛ የሚያስገባ ቢሆንም ከዓለማችን 5 ቀዳሚ ፓስፖርቶች አስተማማኝነቱ በ57 በመቶ ዝቅ ያለ ነው፡፡ የፊንላንድ፣ ስውዲን፣ ዩናይትድ ኪንግደም፣ ጀርመንና አሜሪካ ዜጎች ቪዛ ሳይጠየቁ ወደ 174 የዓለማችን አገራት መግባት ይችላሉ፡፡
ጋምቢያ - ለ68 አገሮች ቪዛ አያስፈልግም
ጋምቢያ በአፍሪካ 5ኛዋ አስተማማኝ ፓስፖርት ያላት አገር ናት፡፡ የጋምቢያ ፓስፖርት ያለምንም ቪዛ 68 የዓለም አገራትን በነፃነት መጎብኘት ያስችላል፡፡
 ኬንያ - ለ68 አገሮች ቪዛ አያስፈልግም
የኬንያ ፓስፖርት በዓለማችን ላይ ወደሚገኙ 68 አገራት ያለ ቪዛ በነፃነት የሚያስገባ ሲሆን እንደ ጋምቢያ ሁሉ በ5ኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ አስተማማኝ ፓስፖርት ነው፡፡
ሌሴቶ - ለ67 አገሮች ቪዛ አያስፈልግም
የሌሴቶ ፓስፖርት በአፍሪካ 6ኛው አስተማማኝ ፓስፖርት ነው፡፡ የሌሴቶ ፓስፖርት የመግቢያ ቪዛ ሳያስፈልግ የዓለማችን 67 አገራትን ለመጎብኘት ያስችላል፡፡
(በነገራችን ላይ የአገራችን ፓስፖርት ያለ ቪዛ መግባት የሚያስችለው ጎረቤት አገር ኬንያ ብቻ ነው።)

Published in ህብረተሰብ

     በ1964፣ 65 እና 66 ዓ.ም በደጀን ትምህርት ቤት በተማሪዎች ዘንድ በእጅጉ ተወዳጅ የነበሩ መምህራንን ሳስታውስ በተለይ እነ ወ/ት ይደነቁ ምትኩ፣ ወ/ት ዘነበች ሥዩም ዋዲሎ ዋዳ፣ አህሙ ደረሩ (የስፖርት መምህር)፣ አበራ ኃይለ ሚካኤል፣ ገብርኤል እምሩ፣ ገበየሁ መንግስቴ፣ ጋሽ ሐሰን፣ ጋሽ ብሩና ጋሽ ንጉሡ ውቤ ተጠቃሾች ናቸው፡፡
በተለይ የሰባተኛና የስምንተኛ ክፍል የሳይንስ አስተማሪዬ የነበረውን መምህር ንጉሡ ውቤን በቅጽል ስሙ “ጋሽ ዝለቀውን” ምንጊዜም አስታውሰዋለሁ። ከትምህርት ቤት ጓደኞቼ ጋር አልፎ አልፎ ስንገናኝም ስለእርሱ ማውራት እንወዳለን፡፡ “ጋሽ ዝለቀው” የተባለውም ጥያቄ ሲጠይቅ፤ “እስቲ ዝለቀው” የሚል ልማድ ስለነበረው ነው፡፡
በ1966 ዓ.ም የ8ኛ ክፍል የሂሳብ አስተማሪ በመጥፋቱ ባዮሎጂ ላይ ደርቦ እንዲያስተምር ተመደበልን፡፡ የክፍላችንም ተጠሪ እርሱ ሆነ፡፡ ጋሽ ንጉሡ አጭርና ወፍራም ሲሆን ፊቱም ክብ ነው፡፡ ሲናገርም በጣም ፈጣን፣ ሳቂታ፣ ቀልደኛም ግልጽም ሰው ነው፡፡ ከቀድሞው የሐረር ጦር አካዳሚ ገብቶ በገዛ ፈቃዱ የወጣ ይመስለኛል፡፡ ብዙ ጊዜ “What is Biology?” እያለ ሲያስተምር፣ ተማሪ ሁሉ ፀጥ ረጭ ብሎ ማዳመጥ አለበት፡፡ በሚያስተምርበት ጊዜ ተማሪ ከተንጫጫ፣ ወይም ከረበሸ አንዴ ወደ መሬት፣ አንዴ ወደ ክፍሉ ጣሪያ፣ አንዴ ወደ እኛ ትላልቅ አይኖቹን እያጉረጠረጠ ብስጭትጭት ይላል፡፡
“…ወይኔ አንበሳው! ይኼኔ ብርጋዴር ጄኔራል ንጉሡ ውቤ በምባልበት ሰዓት የናንተ መቀለጃ ልሁን?” ብሎ ቆጣ በማለት ይናገረንና ወዲያው ሳቅ ይላል፡፡ ጋሽ ንጉሡ አስተምሮ አስተምሮ ጥያቄ መጠየቅና የቤት ስራም ሰጥቶ መቆጣጠር ይወድዳል፡፡ እኛም ማለት አንዳንዶቻችን የእርሱን ሥነ ልቡና በደንብ  እናውቅ ነበር፡፡ ሁልጊዜ እርሱ የሚጠይቀው “እኔ” ብሎ እጅ የማያወጣውንና የማይመልሰውን ነው፡፡ የቤት ሥራ ካልሰራን አውቀን “እኔ እኔ…” ብለን ጥያቄ ለመመለስ እንጫጫለን፡፡ “የለም እናንተማ ጎበዞች ናችሁ፤ እኔ የምጠይቀው እጅ ያላወጡትንና ያደፈጡትን ነው” ይልና ከወንዶች ጥላሁንንና ባንቴን፣ ከሴቶች ደግሞ ዘውድነሽን፣ ኢዛምንና ሺደርብ ጫኔን ይፈልግና “እስቲ እናተ ዝለቁት” ይላል፡፡
የባዮሎጂ ይሁን የሂሳብ ክፍለ ጊዜ ትዝ አይለኝም፤ አንድ ቀን እንደልማዱ ወደ ክፍል በችኮላ እንደገባ፤ “Matter is anything that occupies space….” እያለ ሲያስተምር ቆይቶ፤ “ሺደብር አር ዩ ማተር? (Are you matter?) እስቲ ዝለቂው” ሲል ጠየቃት። ሺደብር የምትቀመጠው እኔ አጠገብ ነበርና “ምንድነው ማተር? ኖ ልበለው ወይስ የስ ልበለው?” ብላ ጠየቀችኝ፡፡ እኔም ተመራመርኩና፤ “መቼም ማተር መጥፎ ወይም ቆሻሻ ነገር ይመስለኛልና ኖ አይ አም ኖት ማተር በይው” አልኳት በለሆሳስ፡፡
“አንችንኮ ነው? ዝለቂው እንጂ” አለ ጋሽ ንጉሡ፤ ፊቱን ከሚጽፍበት ጥቁር ሰሌዳ ወደኛ አዙሮ፡፡ ሺደብርም፤ “ኖ አይ አም ኖት ማተር (I am not matter)” ብላ መለሰችለት፡፡ “እኔን እኔን! ምን ትከፊ ሰው ነሽ አደራሽ፡፡ እንኳን አንቺ ትልቂቱ ሴትዮ ይቅርና ይህች የያዝኳት ጠመኔ እንኳ ማተር ናት” እያለ ስለማተር ምንነት ያስተምረን ጀመር። መምህር ንጉሡ ማስተማሩን ቀጠለና፤ “ነጋቲቭ ኤንድ ነጋቲቭ ሪፔል ኢች አዘር፡፡ ነጋቲቭ ኤንድ ፖዘቲቭ አትራክት ኢች አዘር (Negative plus negative repel each other. Negative and positive attract each other…)” እያለ ሲያብራራ፤ “ጋሸ አልገባንም” አልነው፡፡ ከዚያም ከልጃገረዶች ሺብርን፣ እትየ ይመኑን፣ አስናቀችን፣ ኤልሳቤጥንና ዘውድነሽን፤ ከወንዶች ደግሞ ጥላሁንና፣ ሲሳይን፣ ዘውዱን፣ ፈጠነንና እኔን ተነሱ አለና፤ “በሉ እንግዲህ ሁላችሁም ተመራረጡና ከሴቶች ጋር ተቃፈፉ” አለ፡፡ እኔም በጣም ደስ የምትለኝንና የምወዳትን ኤልሳቤጥ አበበን አቀፍኳት፤ ሌሎችም ወንድና ሴት ሆነው ተቃቀፉና እንደ መደነስ ይቃጣን ጀመር፡፡
“አያችሁ ጎበዝ፤ ነጋቲቭና ፖዘቲቭ አትራክት ኢች አዘር የሚባለው ይኸው ነው፡፡ እርስ በርስ የሚሳሳቡና የሚፈላለጉ ነገሮች ሁሉ አትራክሽን /ስበት/ አላቸው” አለና፤ ወንድ ከወንድ፣ ሴት ከሴት ጋር ደግሞ እንድንተቃቀፍ አደረገ፡፡ “አሁን ደግሞ ሙቀት የለም፤ መሳሳብ የለም፤ መፈቃቀር የለም፤ አለመጣጣም እንጂ” እያለ በመቀለድ ትምህርቱን አስተማረን፡፡
በወቅቱ የሂሳብ መምህርነት የሰለጠነ የ8ኛ ክፍል የሂሳብ አስተማሪ ስለአልተመደበልን መምህር ንጉሡ ሂሳብ ጭምር እንዲያስተምር ተደረገ፡፡ የሂሳብ ትምህርቱ ግን ለአብዛኛው ተማሪ ሊገባን ስለአልቻለ፤ “አንፈልግም ይቀየርልን” ብለን ለርዕሰ መምህሩ ለአቶ ገላጋይ ትርፌ አቤት አልን፡፡ ጋሸ ንጉሱ ወደ ክፍላችን 8ኛ ኤ ገብቶ ሂሳብ ሊያስተምረን ሲል “ውጣልን” አልነው፡፡
“ይህችን ይወድዳል ንጉሡ ውቤ” ብሎ ወደ ዲሬክተሩ ቢሮ ተንደርድሮ በመሄድ፣ አቶ ገላጋይ ትርፌን ይዞ መጣና፤ “እስቲ የኔን የሂሳብ አስተማሪነት የማትፈልጉ እጃችሁን አውጡ! የማትፈልጉ ከክፍሉ መውጣት ትችላላችሁ” አለ፡፡ ወዲያው “ያንተን የሂሳብ አስተማሪነት አንፈልግም” እያሉ አሳምነው አበራ፣ ዳንኤል ታምሩ፣ አብዱ መሐመድ፣ ዘውዱ ዑመርና መዓዛ ታፈሰ ከክፍል ሲወጡ፣ በቁመቱ ረጅምና በዕድሜ ታላቅ የሆነው ባንቴ ጥሩነህ፤ ቀውለል ቀውለል እያለ ሊወጣ ሲል፤ “አንተ ደግሞ የምትወጣው ምን ተበደልኩ ብለህ ነው? ይኼኔ’ኮ ሞሱ ባንቴ የሚባል ልጅ ታደርስ ነበር፡፡” አለው ጋሽ ንጉሡ፡፡ ባንቴ ገራገርና የዋህ ስለነበር ዝም ብሎ ወጣ፡፡
ከዚያ እኔ በእድሜዬም በሰውነቴም ግዙፍነት የተነሳ ከፈጠነ ባንታምላክ ስልጣን ተቀብዬ የ8ኛ ክፍል አለቃ ሆኜ ስለነበር ለመውጣት ስነሳ፣ የቀረውና በቁጥር ስድሳ የሚደርሰው ተማሪ አንዴ ብድግ አለ፡፡ ይህን ጊዜ፤ “አያ ገላጋይ፤ አሁን ገና ያድማው መሪ ተገኘ፡፡ አሳምነው ቢወጣ ማንም አልወጣ፣ አብዱ ቢወጣ ማንም አልወጣ፣ ዘውዱ ቢወጣ ማንም አልወጣ፣ መዓዛ ቢወጣ ማንም አልወጣ፣ አለቃው ሲነሳ ሁሉም ተነሳ፡፡ አቆራኙ እጅ ከፍንጅ ይያዝልኝ” አለ፡፡ ሽደብር ጫኔ አጠገቤ ቆማ ነበርና ወደ እርስዋ እየተመለከተ፤ “አያ ገላጋይ፤ ሺደብር እንኳ ነገሩ አልገባትም፡፡ አሁን ለምንድነው የተነሳሽ? ቢሏት ‹እኔ እንጃ አለቃችን መንክር ስለተነሳ (Because he is the father of the class)› ትላለች እንጂ ሌላ መልስ የላትም” ብሎ ቀለደባት፡፡
ከዚያም የአድማው “መሪዎች” የተባልን ሰባት ተማሪዎች ተመርጠን ስንቀር ሌሎች ወደ ክፍላቸው እንዲገቡ ተደረገ፡፡ እኛም በሰኔ ላይ ለሚተከለው ባሕር ዛፍ አገልግሎት የሚውል መሬት ለሁለት ሳምንታት ያህል በቅጣት መልክ ቆፍረን አለሰለስን፡፡ በመጨረሻ በተሰጠን ምሕረት ወደ ክፍላችን ገባን፡፡ ያን ጊዜ የተማሪ ቅጣቱ “ሥራ” ነበር፡፡
እናም የጋሽ ንጉሱ የሂሳብ አስተማሪነት በርዕሰ መምህሩ ተቀባይነት አገኘና ማስተማሩን ቀጠለ። አንዴ፤ “ኤፍ ኦፍ ኤክስ ፕላስ ኤፍ ኦፍ ኤክስ (F Of X + FOFX) ስንት ነው?” ብሎ በተለይ በሂሳብ ትምህርት ደከም ያሉትን ጥላሁንንና ሺደብርን ሲጠይቅ፤ “እኔጃ” እያሉ መለሱለት፡፡ “አይ የናንተ ነገር፣ ሶስት እንጀራ ሲደመር ሶስት እንጀራ ስንት ነው? ማለት’ኮ ነው፡፡ ኧረ ተዉ ነቃ ነቃ በሉ! የ8ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተናም’ኮ እየተቃረበ ነው” አለ፡፡ እንደአጋጣሚ በዚያው ዓመት የ8ኛ ክፍል ማለፊያ ማርክ 30% ሆነና ጥላሁንና ሺደብር እቅጩን አምጥተው አለፉ፡፡ ጋሽ ንጉሡ ማለፋቸውን እንዳወቀ፤ “ሺደብርና ጥላሁን ጥሩ አምላክ አላቸው” እያለ ያስቀን ነበር፡፡ በዘመኑ በከተማው ውስጥ ፎቶ ቤት ስለአልነበረ ካሜራ ያለው ሰው እንደብርቅ ይታይ ነበር፡፡ በ1966 ዓ.ም ሰኔ ወር ላይ ከደብረ ማርቆስ ፎቶ አንሺ /ፎቶ አምዴ/ ትምህርት ቤታችን ድረስ ስለመጣ፣ ፎቶ መነሳት ብርቃችን ነበር፡፡ ጋሽ ንጉሡም ለማስታወሻ ይሆን ዘንድ የ8ኛ ኤ ተማሪዎች ከአስተማሪዎቻችን ጋር እንድንነሳ አደረገ፡፡ እኛም የእርሱን ትክሻ ተደግፈን የማስታወሻ ፎቶግራፍ ስንነሳ፣ ከሴቶች በጣም ቆንጆዎች የሚባሉት አስናቀች ውብእሸትንና ኤልሳቤጥ አበበን መርጦ ወደራሱ አቀራረባቸው። ሺደብርም አብራቸው ለመነሳት ጠጋ ስትል፤ “ሺደብር አንቺ ቆይ… ፎቶግራፍ ታበላሻለሽ” አለና ቀለደባት፡፡
እርስዋም፤ “እኔ ከማን አንሳለሁ ጋሽ! ቆንጆ ነኝኮ” እያለች በመጠጋት አብራት ተነሳች፡፡ በዚያው በ1967 ዓ.ም ንጉሡ የ8ኛ ክፍል የባዮሎጂና ሂሳብ አስተማሪ ሆኖ ተመድቦ፤ ሸዋየ ታሪኩ የተባለችው ሙዝ ለመንገደኞች እየሸጠች የምትማር ልጅ የሂሳብ ትምህርት ይከብዳታል፡፡ “ኤፍ ኦፍ ኤክስ ፕላስ ኤፍ ኦፍ ኤክስ ስንት ነው?” ሲላት ደንግጣ፤ “ጋሽ ንጉሡ ያንተ ትምርት ከባድ ነው፤ በዚህ ዓይነት 8ኛ ክፍል አልፍ ብለህ ነው!” ትለዋለች፡፡
“ሸዋየ ያንቺ ጠላት’ኮ ኤፍ ኦፍ ኤክስ የሚለው ቃል ነው፡፡ በቀላል አማርኛ 8 ሙዝ ሲደመር 8 ሙዝ ስንት ነው ቢሉሽ መልሱን ቁጭ ነው የምታደርጊው። ስለማለፉ ደግሞ አትጨነቂበት፡፡ አይዞሽ ’የሺደብር አምላክ’ ያውቃል፡፡ ደጉ መንግሥታችን ዘንድሮ ደግሞ የ8ኛን ክፍል ማለፊያ 15% ሊያደርገው ይችላል፡፡ ማን ያውቃል?” ብሎ አስቋታል፡፡
ነፍሱን ይማረውና ጋሽ ንጉሡን አዲስ አበባ አግኝቼው፤ “ጋሽ፤ ምነው ጸጉርህ ሸበተ?” አልኩት፡፡
“አይ ታደለ፤ በእውነቱ አንተም ያንተን ነገር፣ እኔም የእኔን ሽበት አለማየታችን ነው፡፡ እኔም ሽበቴን አንተም መላጣህን የምናይ ቢሆን ኖሮ እንናደድ ነበር፡፡ ደግነቱ ራሳችንን አናየውም፤ ዝንጀሮ የራስዋ መላጣ አይታያትም እንዲሉ” አለና የበለጠ አሳቀኝ፡፡  

Published in ህብረተሰብ
Tuesday, 14 April 2015 08:17

የፀሐፍት ጥግ (ስለምናብ)

ርዕይ የማይታዩ ነገሮችን የማየት ጥበብ ነው፡፡
ጆናታን ስዊፍት
ምናብ ጨርሶ ወደአልነበረ ዓለም ይዞን ይሄዳል፡፡ ያለ እሱ ግን የትም መሄድ አንችልም፡፡
ካርል ሳጋን
ምናቤ አንድ ቀን ወደ ሲኦል የሚያስገባ ፓስፖርት ያመጣልኛል፡፡
ጆን ስቴይንቤክ
(East of Aden)
ምናብ እንደ ጡንቻ ነው፡፡ ብዙ በፃፍኩ ቁጥር እንደሚፈረጥም ተገንዝቤአለሁ፡፡
ፊሊፕ ጆሴ ፋርመር
ምናብህ ከትኩረት ውጭ ሲሆን በዓይንህ ላይ መተማመን አትችልም፡፡
ማርክ ትዌይን
ከምናብ የሚፈጠሩ ታሪኮች ምናብ የሌላቸውን ሰዎች ያበሳጫሉ፡፡
ቴሪ ፕራትሼት
በአቅማቸው ተገድበው የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ በምናብ እጥረት ይሰቃያሉ፡፡
ኦስካር ዋይልድ
በምናብህ መፍጠር የቻልከው ሁሉ እውነት ነው፡፡
ፓብሎ ፒካሶ
ምናብ የሌለው ሰው መብረሪያ ክንፎች የሉትም፡፡
ሙሐመድ አሊ
ምናብ ዓለምን ይገዛል፡፡
ናፖሊዮን ቦናፓርቴ
ሃሳቦችን አፍልቅና በክብር ያዛቸው፤ ከመሃላቸው አንዱ ንጉስ ሊሆን ይችላልና፡፡
ማርክ ቫን ዶሬን
ተጨባጩ ዓለም የሚሸፋፍነውን ሃቅ ልብወለድ ይገላልጠዋል፡፡
ጄሳሚን ዌስት
ምናብ የነፍስ ዓይን ነው፡፡
ጆሴፍ ጁበርት
ዓለምን የሚመሩት ሃሳቦች ናቸው፡፡
ጄምስ ኤ.ጋርፊልድ

Published in ህብረተሰብ
Page 11 of 17