በአንድ ወቅት በዚሁ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ሀገር መውደድ ማለት ባንዲራ ሲያዩ እምባ ማቅረር፤ ጦር ይዞ “ኧረ ጐራው” ማለት እንዳልሆነ ጠቅሼ ይልቁንም ይልቅ ሀገር መውደድ ማለት በሥራ ቦታ፣ በተሰጠን ሃላፊነት ወገንን በፍቅርና በታማኝነት ማገልገል ነው ስል ቁጭቴን ገልጬ ነበር፡፡ እውነትም ሀገርን መውደድ የሚለካው የወገን ሰውን ችግር በመካፈል ጉድለቶቹን ተጋግዞ በመቀነስና በማሻሻል ነው፡፡ ሰሞኑን በሥራ ጉዳይ ሣይሆን በቤተሰብ ጉዳይ ሁለት ሆስፒታሎችን በተከታታይ ቀናት ለማየት ተገድጄ ነበር፡፡ ታዲያ ወዲያ ወዲህ ማለቱ ቢያስመርረኝም በሕክምና ተቋማቱ መልካም አገልግሎት ግን በእጅጉ ተደስቻለሁ፡፡

በሚያሣዝነውም ቅር ተሰኝቻለሁ፡፡ ጐበዝ ያገር ሰው ላገር በጐ ሲሆን ደስ ይላል! የመጀመሪያና የቀጣዩ ቀን ውሎዬ በቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሲሆን ስለ አንዲት ዶክተር በብዙ ሰዎች የሚወራውን ሰምቼ ጆሮዬን ደቅኜ ዋልኩ፡፡ ዶክተር ጥሩወርቅ ትባላለች፡፡ እስካሁን በአካል አላየሁዋትም፤ ግን ከአንድ ተዋናይ ወዳጄ ጋር ወሬ ውስጥ ሆኜ ሁሉም ወንበር ላይ የተደረደሩ ታካሚዎች “ጐበዝ ሰው ናት፤ ጥሩ ሰው ናት” ሲሉ ሰማሁ፡፡ ትንሽ አደመጥኩ። በተለይ ሀኪሞች ጥሩ ሲሆኑ ታካሚዎች በፍቅራቸው ብቻ ሰላም ይሰማቸዋልና ደስ አለኝ፡፡ የሚታከመውም፣ የሚያክመውም ወገን ነውና ጥሩ ስሜት ይፈጥራል፡፡ ለኔ ብቻ ሳይሆን ሀገሩን ለሚወድድ ሁሉ! ሀገር መውደድ የሚገለፀው፣ ሲያገኙ በመሣቅና በመዘመር ሲያጡ ደግሞ በመራገም አይደለም። በመሥራት ነው፡፡ ይህ ደግሞ የለውጥ አምጪ መሪዎች ሚናም /Transformational leaders/ ይመስለኛል፡፡

በቅዱስ ጳውሎስ ያሳዘነኝም ነገር አለ፡፡ ኢንዶስኮፒ ክፍል ካሉ ሴቶች አንድዋ ክፉኛ ሰዎችን ታመናጭቃለች፡፡ ምናልባት ከባለቤትዋ ተጣልታ ወይም ሌላ ችግር ገጥሞዋት ይሆን? ብዬ አሰብኩ፡፡ በማግስቱም ያው ናት፤ ይህ ደስ የሚያሰኝ አይደለም፡፡ ወደ ሁለተኛው ተቋም/ሆስፒታል ልምጣና ጥቂት ልበል፣ በፍፁም የማላምነውን ነገር ነው ያየሁት፡፡ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ለአምስት ቀናት ያህል ተመላለስኩ፤ ማለቴ ሰዓታት አሣለፍኩ፡፡ ግና ተገረምኩ፡፡ የቆየሁት ኢንዶስኮፒና አልትራሳውንድ ክፍል ነው። አይኖቼን ተክዬ፣ ጆሮዎቼን ስዬ ለትዝብት ተመቻቸሁ፡፡ በአብዛኛው ወጣት ሴቶች ናቸው - ሕመምተኞችን የሚቀበሉት፡፡ እመኑኝ ፍቅራቸው የቤተክርስቲያን እንጂ የሆስፒታል አይደለም፡፡ ቤተክርስቲያን ስል የጥንቷን ማለቴ ነው - በመጽሐፍ የምናውቃትን፡፡

አሁን አሁን ቤተክርስቲያን መናከሻ ሥፍራ የንግድ ተቋም እየሆነች ነውና፡፡ በሆስፒታሉ ግን ሰው ሲቀበሉ በፍቅር፣ ሲጠይቁ በፍቅር ነው፡፡ የሚገርም አገልግሎት ነው! በልቤ ሀገር መውደድ ይህ ነው አልኩ፡፡ ሌላው በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የገጠመኝ ተመሳሳይ ነገር የበለጠ ልቤን ገፋፍቶታል። ኮሪደር ላይ ቆሜ ወደ ላይና ወደታች የሚፈስሰውን የሰው ወንዝ ሳይ፣ አንድ በአካል የደከሙ ሰው “211 ቁጥር የት ነው?” ብለው ጠየቁኝ፡፡ እኔ አላውቀውምና በጐናችን ወደሚያልፈው ሃኪም አሳየኋቸው፡፡ ሃኪም ያልኩት ነጭ ጋወን ስለለበሰ ነው፡፡ እሱን ጠየቁት፤ ከዚያ ከሚሄድበት መንገድ ተመልሶ ሊያሳያቸው ሲል “ለኔ አሳየኝና ላሳያቸው” አልኩት፡፡ አሳየኝና ቅር ሲለው ተመልሶ መጣ፡፡ እውነትም እኔ ላገኘው አልችልም ነበር፡፡ በዚህ በዚህ ቀሽም ነኝ! ግን ደስ አይልም…? መማርም እኮ ወገንን ለመርዳት ነው፡፡ እውነት ለመናገር የሰውን ልጅ የሚያረካውም ይኸው ይመስለኛል፡፡ ለሀገርና ለወገን በጐ ነገር ከማድረግ በላይ ምን አለ? … በኔ እምነት ትልቅ ነገር ነው፡፡ በጣም ደስ ይላል። ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ውስጥ ሁሉንም ባይሆን ይህንን እንኳ አይቻለሁና ባየሁት ደስ ብሎኛል! ብልስ?!

Published in ህብረተሰብ

የሰሞኑ የከተማችን አብይ አጀንዳ የገቢዎችና የጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ሃላፊዎችና ትላልቅ ባለሃብቶች በሙስና ተጠርጥረው መያዛቸው ነው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው የፌደራል ሥነ ምግባር እና ፀረ - ሙስና ኮሚሽን፣ የስነምግባር ትምህርት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ከሆኑት አቶ ብርሃኑ አሰፋ ጋር በወቅታዊ የሙስና ጉዳዮች ዙሪያ ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡ የሙስና ድርጊቶች እየተባባሱ መምጣታቸውን የሚናገሩ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ? የሙስና ተግባር በአለም አቀፍ ደረጃ ነው የሚታየው፡፡ ድንበር ተሻጋሪ ነው፡፡ በአንድ አገር ብቻ ተወስኖ የሚቀርብ ችግር አይደለም። ከሽብርተኝነት ቀጥሎ ሙስና አገርን የሚጐዳ እና እያሳሰበ ያለ ተግባር ነው፡፡ ዛሬ በዓለም ላይ የሚከናወኑ የእርዳታ እና የብድር ጉዳዮች እንዲሁም የንግድ ኢንቨስትመንቶች ሁሉ ከፍተኛ የገንዘብ እንቅስቃሴ የሚካሄድባቸው ናቸው፡፡ ከዚህ አኳያ ሙስና እንዳይስፋፋ አለም በደንብ ተጠናክሮ መስራት አለበት፡፡ ከዛ ውጪ በሙስና የተገኙ ገንዘቦች ህገወጥ በሆነ መንገድ ለተለያዩ ስራዎች የሚውሉበት ጊዜ አለ፡፡ አንዳንዴ ለሽብር ተግባር ሊውል ይችላል፡፡

ስለዚህ ከአለም አኳያ ስናየው የአለምን አጠቃላይ ሁኔታ ሊያናጋ የሚችል መሆኑን ሁሉም ተረድቶታል፡፡ በርካታ ስምምነቶች እየወጡ እየተሠሩበት ይገኛል፡፡ እኛ አገርም ስንመጣ ይሔ የሙስና ተግባር ትኩረት ካላገኘ አደጋ መሆኑ በመንግስት ታምኖበታል፡፡ የመንግስት የመልካም አስተዳደር ግንባታ ስራዎች ስኬታማ ሊሆኑ የሚችሉት ሙስናን መከላከል ስንችል ነው፡፡ ከድህነት ለመውጣት የምናደርገውን ጥረት ያደናቅፋል፡፡ ሙስና ለመብራት፣ ለውሀ፣ ለስልክ፣ ለት/ቤት በአጠቃላይ ለመሠረተ ልማት ግንባታና ለህብረተሠቡ የኑሮ መሻሻል የምናደርጋቸውን እንቅስቃሴዎች በተለያየ መንገድ ይጐዳል፡፡

የዲሞክራሲ ስርአት፣ የህግ የበላይነት፣ የመንግስት ተጠያቂነትና ሁሉም በህግ ፊት እኩል እንዳይሆን የማድረግ ተጽእኖም አለው። አንዳንድ ግለሰቦች በሀቅ ማግኘት ካለባቸው ውጪ ያለ አግባብ እንዲበለጽጉ ያደርጋል፡፡ ይሔ ሁሉ ተደምሮ ከድህነትና ከችግር እንዳንወጣ መሰናክል ይሆንብናል፡፡ መንግስት ይህንን በመመልከት ነው በክልል ደረጃ ዘጠኝ የሚሆኑ ቅርንጫፎችን በመክፈት፤ በፌደራል ደረጃ የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ያቋቋመው፡፡ ኮሚሽኑ ማስተባበር እና መምራት ነው እንጂ ሁሉን ነገር ተክቶ አይሠራም፡፡ ከሚዲያ፣ ከሀይማኖት ተቋማት፣ ከሙያ ማህበራት፣ ከንግዱ ማህበራት፣ እንዲሁም መንግስታዊ ካልሆኑ ተቋማት ጋር ግንኙነት እየፈጠርን መንግስትና ህዝቡ በጋራ የሚሠሩበትን ሁኔታ እያመቻቸን ነው፡፡ የባለሥልጣናትን ሃብት መዝግቦ ይፋ የማድረግ ሂደቱ ዘግይቷል ይባላል? ሀብትና ንብረትን ማሳወቅ ሲሆን ሙስናን ከመከላከል ተግባራት አንዱ ነው፡፡ እንግዲህ ከሁለት አመት ተኩል ጀምሮ ወደ 50ሺህ የሚሆኑ ሀብት ንብረታቸውን ማስመዝገብ የሚገባቸው ሠዎችን መዝግበናል፡፡ መረጃቸውን በሀርድ ኮፒ (በማንዋል) ለማዘጋጀት አስበን እየሠራን ነው፡፡

በዚህ በኩል ብዙ ጥያቄዎች እንዳሉ እናምናለን፤ ነገር ግን ኮሚሽኑም ይሔንን ሀብት ይፋ የማድረጉን ስራ በኢንተርኔት ለማንኛውም ሠው እንዲደርስ ነው ስትራቴጂ የቀየሠው፡፡ ይሔ ሲሆን በቀላሉ ማንም ሠው መረጃውን ማግኘት ይችላል፡፡ መረጃ ለህብረተሠቡ የሚሠጠው ያለ ምክንያት አይደለም። ያልተመዘገቡ ሀብትና ንብረቶች ካሉ፣ ምንጩ ያልታወቀ ሀብትና ንብረት እንዲያሳውቅ ለማድረግ ነው፡፡ ከህብረተሠቡ የሚደበቅ ነገር የለም፡፡ ቢዘገይም ከአለም ባንክ ጋር በመተባበር ይሔንን ስራ ለማካሔድና ግዢ ለማከናወን በእንቅስቃሴ ላይ እንገኛለን፡፡ እስከዛ ግን በማንዋል ደረጃም ቢሆን መረጃ ሲጠየቅ እንሰጣለን፡፡ እስካሁንም የሀያ ሶስት ሠዎችን መረጃ ተጠይቀን የሠጠንበት ሁኔታ አለ፡፡ እኛም ለምርመራ እነዚህን ሠነዶች እየተጠቅምን ነው፡፡

ቀደም ሲል ካሠብነው በላይ ነው የተመዘገበው፡፡ እኛ ያሠብነው 22ሺህ ነበር፤ አሁን ግን 50ሺህ ሠዎች ተመዝግበዋል፡፡ ይሔ አሠራር ለእኛ አዲስ ነው፤ ስለዚህ ከሌሎች አገራት ልምድ በመውሠድ እየሠራን ነው፡፡ በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ከፍተኛ ሃላፊዎችና ባለሀብቶች ላይ ያደረጋችሁት ምርመራ አንድ አመት ተኩል የፈጀ ነው ተብሏል፡፡ እንዴት ይሔን ያህል ጊዜ ሊወስድ ቻለ? የምርመራው ሒደት እንዴት ተከናወነ፣ ለምን ተከናወነ የሚለውን ብዙም አላውቅም፡፡ ነገር ግን በዚህ ረገድ የሚከናወኑ የሙስና ወንጀሎች በጣም ውስብስብ እንደሆኑ መረዳት ይቻላል። ተጠርጣሪዎቹ ከፍተኛ ባለስልጣናት ያሉበት በመሆኑ ብዙ ጊዜ ይወስዳል፡፡ ከዛ ውጪ ትልቅ የሙስና ድርጊት ነው ብለን ስለምናምን፣ ጉዳዩን በጠንካራ ማስረጃ ላይ ተመስርቶ ለማቅረብ፣ በፍ/ቤትም የተሻለ ውጤት ለመፍጠር ታስቦ የተካሔደ ምርመራ መሆኑን አውቃለሁ፡፡ ከዛ ውጪ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር ክቡር አቶ መለስ ዜናዊ የሚከታተሉት የምርመራ ጉዳይ ነበር፡፡

እሳቸው ምርመራው ወደ መጨረሻ ደረጃ ላይ ሲደርስ ከዚህ አለም በሞት መለየታቸው እና ከዛ በኋላም ደግሞ የመተካካቱ ሒደት ስራው በፍጥነት እንዳይካሔድ የራሱ አስተዋፅኦ ነበረው፡፡ በዚህ ምክንያት ሰባት ስምንት ወር ዘግይቷል፡፡ የሰሞኑ ባለስልጣናትና ባለሀብቶች የተጠረጠሩበት የሙስና መጠን ከፍተኛ ነው ይባላል፡፡ ከፍተኛ ሲባል ምን ያህል ነው? እስካሁን የምርመራ ስራዎቻችንን አላጠናቀቅንም፡፡ ቢያንስ ምርመራውን ሊያጠናክሩና ክስ ሊያስከስሱ የሚችሉ መሠረታዊ ጭብጦችን የሚያስይዙ መረጃዎችና ማስረጃዎች እንደተሠበሠቡ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን ተጨማሪ ምርመራ የሚፈልጉ ነገሮች አሉ፡፡ የሠው ምስክር ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህን በማጠናከር ላይ ነው የምንገኘው፡፡ ስለዚህ ጥፋቶች በማን ተፈፀሙ፣ ማን በምን መልኩ የሚለውን በዝርዝር ምላሽ የምናገኘው ወደፊት ነው፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ግን ይሔንን ሁሉ ጊዜ ተወስዶ የተመረመረ መሆኑ በራሱ የጉዳዩን ትልቅነት የሚያሳይ ነው፡፡ ዝርዝር ጉዳዩን ማወቅ የሚቻለው ግን ወደፊት በፍርድ ሒደት ነው፡፡

የተጠርጣሪዎቹ የሀብት መጠን ተመዝግቧል? ሀብት የማስመዝገብ ሀላፊነት የተጣለባቸው ወገኖች፣ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ሠራተኞችን ሃብት እንደመዘገቡ አውቃለሁ፡፡ አካባቢው እና ዘርፉ ለሙስና የተጋለጠ በመሆኑ ሁሉም እንደተመዘገቡ እርግጠኛ ነኝ፡፡ ሌሎቹ ግን ባለሀብቶች ናቸው፡፡ የግል ንግድ ላይ የተሠማሩት ስለማይመዘገቡ የእነሱ አይታወቅም፡፡ የሀብታቸውን መጠን ማወቅ ይቻላል? በአሁኑ ጊዜ ማሳወቅ ይከብዳል፤ ወደፊት ይፋ ይሆናል፡፡ “ግንዱ አልተነካም ቅርንጫፉም ጥቂቱ ነው የተነካው” የሚሉ ወገኖች አሉ … በመጀመሪያ ደረጃ እኛ የምንይዘው ሠውን አይተን አይደለም፡፡ እኛ የምናየው ምን አይነት የሙስና ወንጀል ወይም ድርጊት ተፈፅሟል የሚለውን ነው፡፡ ኮሚሽኑ ከዚህ በፊትም ቢሆን ከፍተኛ ባለስልጣናት እንዲጠየቁ የሚያደርግበት አሰራር ነበረው፡፡

እነዚህ ሠዎች የሚጠየቁት ከፍተኛ ባለስልጣናት ስለሆኑ ሳይሆን የሙስና ወንጀልን ስለፈፀሙ ነው፡፡ ትንሽም ይሁን ትልቅ ባለስልጣን መነሻችን ይሔ ነው፡፡ ከህግ በላይ የሆነ የለም፡፡ ከዚህ በፊትም ይሔንን ስናደርግ ነበር። ምናልባት በአሁኑ ሠአት በህዝቡ ውስጥ የተለየ ስሜት ፈጥሮ ሊሆን ይችላል፡፡ አሁን በመልካም አስተዳደር ችግሮች ለየት ባለ መልኩ የህዝብ እሮሮ በማየሉ ሊሆን ይችላል። አሁን የተያዙት ቅርንጫፎቹ ናቸው ግንዶቹ አይደሉም ያሉት። እንግዲህ ከሚኒስትር በላይ ግንዱ የቱ እንደሆነ ቢነግሩን ጥሩ ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ እኛ የሙስና ወንጀል እስከተፈፀመ ድረስ ማንንም በህግ እንጠይቃለን፡፡ ፀረ-ሙስና ከዚህ በፊት ትልልቅ ባለሥልጣናትን ለምን እንደማይከስ ተጠይቆ፣ በእኛ አገር እየታየ ያለው ሙስና በጣም ጥቃቅን ነው የሚል መልስ ሠጥቷል፡፡ አሁን ባለው ሁኔታስ ትልልቅ ሙስናዎች እየተፈፀሙ ነው ለማለት ያስችላል? ኮሚሽኑ ትልቅ የሙስና ወንጀል እኛ አገር የለም ብሎ የተናገረበትን ጊዜ አላስታውስም። እኛ አገር ትላልቅ የሙስና ወንጀሎች አሉ፡፡ አጋጥሞን መርምረን ለህግ ያቀረብንበት ጊዜ አለ።

የአሁኑም ተመሳሳይ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ከወርቅ ማጭበርበር ጋር ተያያዞ 153 ሚሊዮን ብር፣ በቴሌ የግዢ ጨረታ 1.8 ቢሊዮን ብር እንዲሁም በመሬት አስተዳደር ላይ ያደረግናቸው እንቅስቃሴዎች አሉ፡፡ ከዛ በኋላም የኤሌክትሪክ ሀይልን ቆጣሪ በማዘዋወር ከ60 ሚሊዮን ብር በላይና ከአገር ሊወጡ የነበሩ ወርቆችን የመሳሰሉ ትላልቅ የሙስና ወንጀሎችን መርምረናል። ሠርተናል፡፡ አንዳንድ ጊዜ እንደዚህ አይነት ሙስናዎች በትላልቅ ባለስልጣን መፈፀማቸው ወይም የገንዘቡ መጠን “ግራንድ ኮራፕሽን” ሊያሠኝ ይችላል፡፡ አንዳንዴ በአገሪቱ ደህንነትና ፀጥታ ላይ የሚያደርሠው ጉዳትም “ግራንድ ኮራፕሽን” ያሰኘዋል፡፡ አሁንም ትላልቅ ባለስልጣናት ላይ የሠራናቸው ምርመራዎች አሉ። ቁምነገሩ ትላልቅ ሙስናዎች አይፈፀሙም ሳይሆን የትኛው ይበዛል የሚለው ነው፡፡ ጥናቶች እንደሚያሳዩት፤ በአብዛኛው በኢትዮጵያ ውስጥ አነስተኛ ሙስና የምንላቸው ጐልተው ይታያሉ።

በቅርቡ ያካሔድነው የኢትዮጵያ የሙስና ቅኝት ጥናት የሚያሳየው፤ አነስተኛ ሙስና እንደሚበዛ ነው፡፡ አነስተኛ ሲባል ግን እያቃለልነው አይደለም። አብዛኛውን የህብረተሠብ ክፍል መቀነት የሚያስፈታና መከራ የሚያሳይ፣ በአገልግሎት አሠጣጥ ላይ እንዲጐሳቆል የሚያደርግ የሙስና አይነት ነው፡፡ ስለዚህ አነስተኛው ተብሎ የሚናቅ አይደለም፡፡ ብዙ ጊዜ የሚከሠቱትና ብዙዎቻችንን የሚያስለቅሱት እንደዚህ አይነት ሙስናዎች ናቸው። ሌላም አገር ብትሔጂ ትልልቅ ሙስናዎች በየዕለቱ አይፈፀሙም፡፡ ለዚህ ይሆናል ህብረተሠቡ ትልልቅ ሙስናዎች ላይ አታተኩሩም የሚለው፡፡ እለት በእለት እየተፈፀሙ ያሉት አነስተኛ የምንላቸው ናቸው፡፡ ለሙስና ተጋላጭ ከሆኑ ተቋማት በቀዳሚነት የምትጠቅሱት ጉምሩክን ነው፡፡ ሁለተኛስ? ገቢዎችና ጉምሩክ ለሙስና የተጋለጠ አካባቢ ነው ስንል፣ አንዳንዶች ሠራተኞቹ በሙስና የተዘፈቁ እና በሙስና የተጨማለቁ አድርገው ይወስዱታል። ይሔ ትክክል አይደለም፡፡

ለሙስና የተጋለጡ የምንላቸው፤ ጥንቃቄ ልናደርግባቸውና አይናችንና ሁለንተናችን ሊያርፍባቸው የሚገባ አሳሳቢዎቹ ቦታዎች ለማለት ነው፡፡ ከእነዚህ አካባቢዎች አንዱ ገቢዎችና ጉምሩክ ነው፡፡ በመቀጠል የኮንስትራክሽን ዘርፍ፣ ትልልቅ የመንግስት ግዢዎች፣… ቴሌኮም፣ የሀይል አቅርቦት፣ የመሬት አስተዳደር፣ ፍቃድ ሠጪ አካላትና የፍትህ አካላት… ለሙስና የተጋለጡ ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ በአገራችን የተሰሩ አንዳንድ ጥናቶችም የሚያሳዩት እነዚህ አካባቢዎች ለሙስና የተጋለጡ መሆናቸውን ነው፡፡ ተጠርጣሪዎቹን በምትይዙበት ወቅት የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ መላኩ ፈንቴ የአዲስ አበባ መስተዳድር ምክር ቤት አባል መሆናቸውን አታውቁም ነበር? በእኛ እምነት ተጠርጣሪው ይሔንን ቢገልፁልን ጥሩ ነበር፡፡ ሆኖም ቅሬታቸውን አቅርበው ፍ/ቤት ለግንቦት 19 ማስረጃቸውን እንዲያቀርቡ አዟል። እኛ ያው ህግን ተከትለን ነውና የምንሠራው ምን እንደሚሆን ወደፊት እናያለን፡፡

በእኛ በኩል መርመሪዎቻችን ይወቁ አይወቁ ገና አላወቅሁም። ግን አባል ከሆኑም ምን ይደረጋል የሚለውን እንወስናለን፡፡ ጥያቄው ከመብት ጋር የሚያያዝ ነው፡፡ እኛ ግን ምርመራችንን እንቀጥላለን፡፡ አባልነታቸው ከተረጋገጠ ክሱ ይቋረጣል? አይቋረጥም፡፡ ከዚህ በፊትም አጋጥሞናል። ለምሳሌ የቤንሻንጉል አፈ ጉባኤ ያለመከሠስ መብት አላቸው፡፡ ያንን መብታቸውን የማስነሳት አግባብ ስላለ፣ ያንን በማድረግ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት ወስደናል፡፡ በአሁኑ ሁኔታ ግን ገና ምርመራ ላይ ነን። ክስም አልተመሠረተም፡፡ በአገሪቱ የሚፈፀሙትን የሙስና ወንጀሎች በሙሉ የመመርመር አቅም አላችሁ? የአቅም ጉዳይ በብዙ መንገዶች ይከፈላል። የሠው ሀይል ሊሆን ይችላል፡፡ የማቴሪያል ጉዳይ ሊሆንም ይችላል፡፡ ከሙስና ጋር የተያያዙ ነገሮችን ለመመርመር አቅም ያንሰናል የሚል ሀሳብ የለኝም። ነገር ግን የተሟላ ነገር አለን ለማለት አልችልም። የማስፈፀም ችግሮች በሁሉም በኩል የሚታዩ ናቸው፡፡ በእኛም በኩል ይሔ ችግር የለም ብሎ መደምደም አይቻልም፡፡ በአንድ ቦታ ያለን አቅም፣ በሌሎች ተለዋዋጭ ቦታዎች ላይሠራ ይችላል።

አቅም የመገንባቱ ስራ የማያቋርጥ ነው። በአንዱ ነገር አቅም ቢኖረን በሌላው ነገር ደግሞ ክፍተት ሊኖር ይችላል፡፡ አቅም አንዴ የሚገነባ ነው ማለት አይቻልም፤ ነገር ግን አሁን ባለንበት ሁኔታ ጥሩ የሆነ አቅም አለን፡፡ በተጨማሪ ደግሞ ከዚህ በፊት እንዳደረግነው ከሌሎች መንግስታዊ መ/ቤቶች ጋር በመቀናጀት እንሠራለን፡፡ የመረጃ ልውውጥ እናደርጋን፡፡ ለምሳሌ ከፖሊስ፣ ከመረጃና ደህንነት፣ ከዋና ኦዲተሮች ጋር የምንሠራበት ጊዜ አለ፡፡ ኦዲተሮች የእነሱን ሙያ የሚጠይቁ ነገሮች ኦዲት አድርገው እንዲልኩልን እናደርጋለን፡፡ አስፈላጊ ከሆነም የሌሎችን አቅም እንጠቀማለን። ይሔንን በማጠናቀር የበለጠ ሀይል በመያዝ የተለያዩ ስራዎችን እንሠራለን፡፡ ህብረተሠቡም አንዱ ሀይላችን ነው፡፡ ጥቆማ የሚሰጠውና ምስክር የሚሆነው ህብረተሠቡ ነው፡፡ ስለዚህ አቅም የሚባለው ነገር በዚህ በኩል እየተገነባና እየተሠራ የሚሔድ ነው፡፡ የአሁኑ ተጠርጣሪዎችን ጉዳይ ወደ እናንተ ያመጣው ግለሠብ ነው ወይስ ተቋም? ጥቆማውን ማን ሠጠው የሚለውን ነገር ለመናገር ይከብዳል፡፡ ነገር ግን ለእኛ ነው መጀመሪያ የተነገረን፡፡ ስለዚህ ይሔንን ሁኔታ ለማየትና ከሌሎች አካሎች ድጋፍ ለማግኘት ከቀድሞ ጠ/ሚ አስፈላጊው መመሪያ እንዲሠጥ አድርገን፣ በጋራ ስንሠራ ነው የቆየነው፡፡

በጥንቃቄ ለመሠራቱ ማሳያው አብዛኛዎቹ ተጠርጣሪዎቹ በስራ ገበታቸው ላይ እንዳሉ ነው የተያዙት፡፡ እኛ በቂ መረጃ እስኪኖረን ድረስ ምንም አይነት ነገር ማድረግ ስላልፈለግን ስራቸውን እንዲሠሩ ትተናቸው ነበር፡፡ ኮሚሽኑ ሌሎች ከፍተኛ ባለስልጣናትን ለመመርመር ድፍረት አግኝቷል ወይስ አሁንም ጠ/ሚኒስትሩን ማስፈቀድ አለባችሁ? ድሮም የሙስና ወንጀል በማንም በምንም ይፈፀም ድፍረት ያጣንበት ጊዜ የለም፡፡ ሠዎች እንደዚህ አይነት ሀሳብ ሊኖራቸው ይችላል። እኛን የሚያሳስበን ግን ሠዎችን ለመያዝና ወደ ህግ ለማቅረብ በቂ ማስረጃ አለን ወይ የሚለው ነው። ድፍረታችን የሚወሰነው ባለን ማስረጃ ነው። ሠዎችን ደፍረን ለመጠየቅና ፍ/ቤት ለመውሠድ የሚያስችለን ማስረጃ ካለን ምንም የሚያስፈራን ነገር የለም። በዚህ ሁኔታም ከዚህ በፊት ጠይቀናል። አሁንም ከፍተኛ ባለስልጣንን እየጠየቅን ነው። ነገም ማስረጃ ካለን እንጠይቃለን፡፡ ሌላው እኛ ማንንም ሠው ለመያዝ ጠ/ሚኒስትሩን አንጠይቅም። ምናልባት ጠ/ሚኒስትሩን ጠየቀን ያልነው፣ ሌሎች አካላት ድጋፍ እንዲሰጡን ከማድረግ አኳያ እንጂ እኛ ነፃነት አለን፡፡

በኮሚሽኑ አዋጅ ውስጥ በምርመራ ሁኔታ ላይ ያለማንም ጣልቃ ገብነት መስራት እንዳለብን ይደነግጋል፡፡ እስካሁን ጣልቃ ገብቶ ይሔንን አድርግ ያለን አካል የለም፡፡ ከተቋቋማችሁ ጊዜ ጀምሮ ከፍተኛ ምርመራ ጠይቆ የተሠራው የሙስና ወንጀል የአሁኑ ነው ማለት ይቻላል? በእኛ እምነት አሁን እያደረግን ያለነው እንቅስቃሴ ትልቅ ድል ነው፡፡ በፍ/ቤት ተከራክረን በመርታት አጥፊዎች ተገቢውን ቅጣት አግኝተው ያለ አግባብ የተወሠደው የመንግስትና የህዝብ ሀብት እንዲመለስ በማድረግ፣ ሂደቱን በውጤት ስንቋጨው ትልቅ ከሚባሉ የሙስና ወንጀሎች አንዱ እንደሚሆን እርግጠኛ ነኝ፡፡ አንዳንድ ባለሀብት ለስራው የጥሬ እቃ አቅርቦት ያጣና ከውጪ ለማስገባት ሲል ካቅሙ በላይ በሆነ ችግር ጉቦ ተጠይቆ ሊከፍል ይችላል፡፡ ይሄና ያልተገባ ሀብትን ለማፍራት የሚፈፀሙ የሙስና ድርጊቶችን በእኩል ዓይን ነው የምታዩት? ነጋዴው እንዲህ አይነት ችግር ሲደርስበት ሙስና ውስጥ ገብቶ እራሱን፣ ሀብቱንና ቤተሠቡን ችግር ላይ መጣል የለበትም፡፡ እንደ እኛ አይነት አካላት አሉ፡፡ እዛ ሔዶ ችግሩን ማስረዳት እና ችግሩን እንዲፈቱለት ማድረግ እንጂ ወንጀል ውስጥ እየገቡ ተቸግሬ ነው ማለት አያዋጣም፡፡ ይሄ ራስን ለማበልፀግ ካለ ፍላጐት የሚመነጭ እንጂ ምክንያት ሆኖ ሊቀርብ የሚችል አይደለም፡፡

አቶ ሽመልስ ከማል - የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስቴር ሚኒስትር ዲኤታ

   በተለያዩ ማህበራዊ ድረ-ገፆች እንዲሁም በአንዳንድ ፖለቲከኞች ዘንድ ከሙስና ወንጀል ጋር ተያይዞ የታሠሩ ግለሠቦችን በተመለከተ ጉዳዩ የፖለቲካ ነው የሚሉ አስተያየቶች ይሰነዘራሉ፡፡ መንግስት በዚህ ላይ አቋሙ ምንድን ነው? ህብረተሠቡና መንግስት ሙስናን በጋራ ለመከላከል የሚያደርጉትን ጥረት ለማኮሠስ ነው ፖለቲካ ነው የሚባለው፡፡ ይሄን ጥረት ለማክሸፍና ለማምከን የሚደረግ ጥረት ነው፡፡ የተለየ ነገር የለውም፤ በማስረጃ ተደግፎ በጓዳ ሣይሆን በአደባባይ የሚሠራ ነው፡፡

እንዴት ተብሎ ነው ፖለቲካ ነው የሚባለው? የፖለቲካ ተቃዋሚ ፓርቲዎች እየሠጡ ያለውን አስተያየት እየሠማሁት ነው፡፡ እነሡ ሁለት ስለት ያለው ቢላ ነው ያላቸው፡፡ ደስ ሲላቸዉ ሙስናን አልተከላከለም ብለው መንግስትን ይወቅሣሉ፡፡ መዋጋት ሲጀምር ደግሞ ፖለቲካዊ ነው ብለው ያወግዛሉ፡፡ ምንም የማያስደስታቸው፣ በምንም መንገድ ብለው መንግስትን ለማውገዝ የሚጥሩ ናቸው፡፡ ይህን አይነቱን እርምጃ ፖለቲካዊ ነው ብሎ ማለት ለኪራይ ሠብሣቢነት አሠራር ድጋፍ ማበጀት ነው፡፡ ለኪራይ ሠብሣቢዎች ድጋፍ መስጠት ነው፡፡ ይሄ ከኪራይ ሠብሣቢዎች መንደር የሚነሣ ሃሣብ ነው፡፡ ገና ለገና ይመጣብናል ብሎ የሚያስበው ሁሉ ነው ፖለቲካዊ ነው የሚለው፡፡ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ የተናገሩትን ጋዜጣ ላይ አንብቤአለሁ “ሠው እየተደናበረ ነው” ብለዋል፡፡

ማን ነው የሚደናበረው? የተነካካ ነው የሚደናበረው፤ ይመጣብኛል ብሎ የሚፈራው እሱ ነው፡፡ መንግስት ይህን አይነት እርምጃ ሲወስድ የመጀመሪያ ጊዜው አይደለም፡፡ ከዚህ በፊት ከጠቅላይ ሚኒስትር ታምራት ላይኔ ጀምሮ እንደ ስዬ አይነት የመከላከያ ሚኒስትሮች፣ ሌሎችም ሃላፊዎችን በሙስና ባገኛቸው ጊዜ እርምጃ ወስዶባቸዋል፡፡ የእነሡ ጉዳይ ፀሃይ የሞቀው ነው፤ በፍርድ ቤት ተከራክረውበት በማስረጃ ተረጋግጦ የተቀጡበት ነው፡፡ እርምጃው ዛሬ አልተጀመረም፤ በእርግጥ ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበት ነበር፡፡ አሁን መንግስት በአዲስ መልኩ ተጠናክሮ እቀጥላለሁ ብሎ እየሠራ ነው፡፡ በዚህ ዙሪያ በህብረተሠቡ ዘንድ ወጥነት ያለው ብሄራዊ መግባባት ነው የተፈጠረው ማለት ይቻላል፡፡ ሙስና ላይ ለምን መጣችሁ ብሎ የሚኮንነው ወገን ለይቶ ወጥቷል፡፡

ማን ከሙስና ጐራ እንዳለ አሁን ነው የሚለየው፡፡ ሙሠኞችን ነካችኋቸው ብለው ፖለቲካዊ እርምጃ ነው የሚሉ ሠዎች ማህበራዊ መሠረታቸዉ በሙስና የተበደለው ድሃው ህብረተሠብ ሣይሆን፣ በሙስና በአቋራጭ መክበር የሚፈልገው ኪራይ ሠብሣቢ ነው፡፡ በሌላ አባባል እያሉ ያሉት አትንኳቸው፣ አትምጡባቸው ነው፡፡ መንግስት ለምን ፀረ-ሙስና እና ፀረ ኪራይ ሠብሣቢነት ላይ እርምጃ ወሠደ የሚል አመለካከት ነው፡፡ ህብረተሠቡ በሙሉ ልቡ ፖለቲካዊ ድጋፍ ሠጥቶታል፡፡ ተጠናክሮ ይቀጥል እያለ ነው፡፡ ጥቂት ወገኖች ደግሞ ለምን እርምጃ ይወሠዳል ብለው “ቡራ ከረዩ” እያሉ ነው፡፡ የአንደበት ግልጋሎት ሲሠጡ የነበሩ ግለሠቦች፣አሁን ትክክለኛ ስራው ሲጀመር “አትንኳቸው፣ ፖለቲካዊ ነው” የሚሉ አስተያየቶችን በመስጠት ራሣቸው የሞራል ግብረአበሮች መሆናቸውን እያሳዩ ነው፡፡

“ኢህአዴግም እንደ ድርጅት ሙሠኛ ነው” ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ -የመድረክ አመራሮች አባል

የመንግስት መዋቅር በሙስና የተዘፈቀ ነው የሚል ትችት በተደጋጋሚ ትሰነዝራላችሁ፡፡ ኢህአዴግ ዋናዎቹን ትቶ በትናንሽ ሙሰኞች ላይ ነው የሚያተኩረው፣ይህ ደግሞ ሙስናን እየተከላከለ ነው አያሠኘውም ትላላችሁ፡፡ ከዚህ አንፃር ሠሞኑን በገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን ከፍተኛ ሃላፊዎችና ባለሃብቶች ላይ የተወሠደው እርምጃ የዚህ ትችትና ምክር ውጤት ነው ማለት ይቻላል? ይህ እንግዲህ አንደኛ በጣም የገዘፈን ነገር እንዲሁ መነካካት ነው፡፡ ምክንያቱም ኢህአዴግና ስርአቱ፣ አባሎቼና ደጋፊዎቼ የሚላቸው አሉ፡፡ እነሡ ሃገሪቱን በሙሉ እንዲበዘብዙ ድጋፍ ይሰጣቸዋል፡፡

ከዚህ አንፃር የሠሞኑ እርምጃ መነካካት ነው፡፡ ዋናውን የሙስና ሠንሠለት ለመበጣጠስ የጀመረው እንቅስቃሴ ነው ለማለት ገና ነው፡፡ እስካሁን ባሳለፈው 21 የስልጣን አመታት አንዳንዴ በፖለቲካውም በዲፕሎማሲውም ሲጨንቀው ከሹመኞቹ ውስጥ ጭዳ የሚያደርጋቸው አሉ፡፡ እነዚያን እየሠዋ ይሄው እርምጃ እየወሠድኩ ነው፤ በማንም ላይ ቢሆን መረጃ እስካለ ድረስ እርምጃ ለመውሠድ ዝግጁ ነኝ የሚል የፖለቲካ ጨዋታ አለው፡፡ በሽግግሩ ወቅት ከአቶ ታምራት ላይኔ አንስቶ፣ አቶ ስዬ፣ ሌሎቹንም ከህወሃት ጋር የተጋጩትን ሲያስር ሲፈታ ነው የኖረው፡፡ በዚያ ሠሞን ኢህአዴጐች ጉባኤ እያካሄዱ ነበር፡፡ ይህ እርምጃ ደግሞ ከጉባኤው ተከትሎ የመጣ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የፖለቲካ ጉዳይ እንዳለበት ምልክትም ሊሆን ይችላል፡፡ የፍትህ ሚኒስትሩ አቶ ብርሃንም እንዲነሡ ተደርጓል፡፡ የገቢዎች ባለሥልጣን እቃዎችን ከቀረጥ ነፃ የማስገባት ነገር ስላለው ከለጋሾች ጋር ያነካካል፡፡

እናም ጫናውን ትንሽ ለማስተንፈስም ጭምር ያደረጉት ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ ሁሉንም በሂደት የምናየው ይሆናል፡፡ እርምጃው በዚህ ላይ ብቻ የሚቆም ከሆነ በመሠረቱ የሚያደላው ፖለቲካዊ ፋይዳው ነው፡፡ ሙስና እንግዲህ አዲስ አበባንም ሆነ ሌሎች ከተሞችን ያጣበበ ነው፡፡ ሁሉም ጋ ሄደው እርምጃ የሚወስዱ ከሆነ እሠየው የሚያሠኝ ነው፡፡ በኛ እምነት ይሄ ሁሉ ከበርቴ ሚሊየነርና ቢሊየነር ዝም ብሎ እየፈላ ያለው፣ የሃገሪቱን ህዝብ ሃብትና ገንዘብ እየበዘበዘ ነው፡፡ ሙሰኝነቱ ነው አብዛኛውን እዚህ ያደረሠው፡፡ ኢህአዴግም እንደ ድርጅት ሙሠኛ ነው፡፡ ኪራይ ሣይከፍል የሚጠቀምባቸው ትላልቅ ህንፃዎች አሉ፡፡ እነሱ የህዝብ ንብረቶች ናቸው፡፡ ኢህአዴግ ከዋናው ፅ/ቤቱ አንስቶ ሌሎች ስራዎችን የሚሠራባቸውን ቢሮዎች እንደማንኛውም ፖለቲካ ፓርቲ ኪራይ እየከፈለ ነው የሚጠቀመው? ይህ እንግዲህ በምርመራ ጋዜጠኞች መጣራት ያለበት ነገር ነው፡፡

እኔ እስከማውቀው ድረስ ግን እንደማይከፍሉ ነው፡፡ በቅርብ ጊዜ የተለወጠ ነገር ከሌለ እያንዳንዱ የኢህአዴግ ካድሬ ገብቶ የሚኖርባቸው ያኔ ከደርግ የወረሣቸዉ ትልልቅ ቤቶች ኪራይ ይከፈልባቸዋል? እኔ እስከማውቀው ድረስ ሣይከፍሉ ነው የሚጠቀሙት፡፡ መረጃው በጋዜጠኞች ሊቀርብ ይገባዋል፡፡ ቦሌ ያሉ የድሮ ትልልቅ መኳንንት የሠሯቸውን ቪላ ቤቶች፣ ከትግሉ መልስ እየተሽቀዳደሙ እንደገቡበት ነው የምናስታውሠው፡፡ ከዚህ በላይ ሙሠኝነት አለ እንዴ? የህዝብ ንብረት እኮ ነው ወይ ለባለቤቶቹ አልተመለሠ? ኢህአዴግ ሙሠኛ ነው ልንል የሚያስችሉን እነዚህ ነጥቦችና ሌሎችም ናቸው፡፡ ሙሠኝነት በኢትዮጵያ ውስጥ መሠረቱ በጣም ሠፊ ነው፡፡ አደገ የሚባለው ኢኮኖሚ፣ ተሠሩ የሚባሉት ሠማይ ጠቀስ ፎቆች መሠረታቸው ሙሠኝነት ነው፡፡

ከበርቴ ነን ከሚሉት የአንዳንዶቹን መነሻ እናውቃለን፡፡ ራሱ ገዥው ፓርቲ የሚያንቀሣቅሳቸው የኢንዱስትሪና የንግድ ድርጅቶች ሣይቀሩ የሙስና ጉዳይ ያለባቸው ናቸው፡፡ አንዳንድ ወገኖች ዘግይቷል ቢሉም በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣናት ላይ ሰሞኑን የተወሠደው እርምጃ ኢህአዴግ የሙስና ችግሮችን ለማፅዳት መቁረጡን አያመለክትም? በአሁኑ ደረጃ እርምጃ መውሠድ ጀምሯል ማለት አንችልም፡፡ ምክንያቱም አሁንም ትላልቅ አሣዎች አሉ፡፡ በዚህ ዘመን እኮ የኢህአዴግ አባል ወይም ደጋፊ መሆን ማለት ከበርቴ መሆን ነው፡፡ ብዙዎቹ በዚህ መሠረት ተጠቅመዋል፡፡ እንዳሁኑ ዓይነት እርምጃዎች ከቀጠሉ መሠረቱ ሊናጋ ነው ማለት ነው፡፡ ፓርቲው የህዝብ ሃብትን ለራሱ እየተጠቀመ ከመሆኑም በላይ ወዳጆቹን እንዴት እየጠቀመ ነው የሚለውንም ማየት ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ አንፃር ኢህአዴግ ራሱን ማፅዳት ጀመረ ማለት ይቸግራል፡፡ እንዲያ ከሆነ ከውስጥ ትልቅ ቀውስ ተፈጠረ ማለት ነው፡፡

 “ይሄ የዶሮ ትራፊ ነው፤ ትልቁ ገንዘብ የት ነው ያለው?” ኢ/ር ሃይሉ ሻውል -

የመኢአድ ፕሬዚዳንት በሙስና ተጠርጥረው የተያዙት ሠዎች ጉዳይ የፖለቲካ ግንኙነት ያለው ይመስላል፡፡ ይህ ደግሞ አምባገነን መንግስት ባለበት ሁሉ የሚደረግ ነው፡፡ በደርግ ጊዜም የማይፈለግ ሠው እንደዚህ ይደረግ ነበር፡፡ በእርግጥም የተያዙት ሠዎች የተጠረጠሩበት ጉዳይ እውነት ከሆነ እርምጃው ይቀጥላል ብዬ አምናለሁ፡፡ በሙስና የደለቡትን አንስተው ያሣዩን ይሆናል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ነገሩን ሙስና ብቻ ብሎ ለመቀበል ይቸግራል፡፡ በቅርቡ ለፓርላማ በቀረበው ሪፖርት ላይ፣ የፌዴራል ኦዲተሩ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ከፍተኛ የገንዘብ ጉድለት መኖሩን ጠቁሟል፡፡ ዛሬ እነዚህ ሠዎች ቤት አንድ መቶ ሺህ ብር ተገኘ፤ ሲባል ይሄ የዶሮ ትራፊ ነው፤ ትልቁ ገንዘብ የት ነው ያለው? ከዚህ ቀደም የአለም ሚዲያዎች ብዙ ቢሊዮን ዶላር ከሃገር እንደወጣ ነግረውናል፤ እኔ ቁጥሩን አላስታውሠውም፡፡ ይህንንና አሁን የተነገረውን ስናስተያይ ገና ጫፉም አልተነካም፡፡ 

“አሣ ማጥመጃው ትልልቅ አሣዎችን የሚያጠምድ ከሆነ እንተባበራለን” ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማሪያም -

አለማቀፍ የህግ ምሁር በሙስና በተጠረጠሩት ላይ መንግስት በወሠደው እርምጃ ምን አስተያየት አለዎት? የተወሠደው እርምጃ የሚቀጥል ከሆነ በእውነት የሚመሠገን ነው፡፡ የተወሠደው እርምጃ ግን ካለው ሁኔታ ጋር ሲመዛዘን ኢምንት ነው ማለት ይቻላል፡፡ አሁን የታየው ኢምንቱ ነው፡፡ ይህ ተጠናክሮ የሚቀጥል ከሆነ እሠየው የሚያስብል ነው፡፡ ለዚህ ሁሉም ኢትዮጵያዊ መተባበር አለበት፡፡ ለፖለቲካ ጥቅም ወይም በፖለቲካ ግጭት ምክንያት የተፈጠረ ከሆነ ግን ለኢትዮጵያ ህዝብ የሚጠቅመው ነገር የለም፡፡ ዝም ብሎ ጊዜ ማባከን ነው፡፡ መዘንጋት የሌለበት ግን ከእነዚህ የበለጡ ትላልቅ አሣዎች ዛሬም አሉ፡፡ እነዚህ አሣዎች እስካሁን ድረስ አልተነኩም፡፡ አሣ ማጥመጃው እነዚህን ትልልቅ አሣዎች የሚያጠምድ ከሆነ፣ እኛም እሠየው ብለን እንተባበራለን፡፡ አንዳንዶች የጉምሩክ አሠራር በራሱ ለሙስና ምቹ ነው ይላሉ፡፡ እርስዎስ? በእርግጥም ጉምሩክ አሠራሩ በራሱ ለሙስና በር ከፋች ነው፡፡ ራሱ ከሣሽ ነው፣ ዳኛ ነው፡፡ መጀመሪያውኑ ለሙስና አመቺ ሆኖ የተዋቀረ ነው፡፡ ያዋቀሩት ሠዎች ግልፅ ባልሆነ መንገድ የህዝቡን ሃብት ለመንጠቅ ያደረጉትም ሊሆን ይችላል፡፡ እርግጥ ነው አሁን መንግስት ይህን ነገር ማጥፋት ከፈለገ መዋቅራዊ ለውጥ ማድረግ አለበት፡፡ መዋቅሩን በሙሉ መለወጥ አለበት፡፡ አንድ ሁለት ሠው በመክሠስ ብቻ ችግሩ የሚወገድ አይደለም፡፡ ሃገራችን ከዚህ ቀደም ሙስናን በተመለከተ በአለማቀፍ ደረጃ በጣም ጥሩ ሪከርድ ነበራት፡፡ አሁን በትራንስፓረንሲ ኢንተርናሽናል አመዘጋገብ ወደ 3ኛ ደረጃ ተጠግታለች፡፡ ይሄ በጣም አሣፋሪ ነው፡፡

“ገቢዎች ከመንግስትም በላይ ስልጣን የተሰጠው አካል ነው” አቶ ሙሼ ሠሙ - የኢዴፓ ሊቀመንበር

ፀረ ሙስና ኮሚሽን ሰሞኑን በሙስና በጠረጠራቸው ትላልቅ ባለስልጣናትና ባለሃብቶች ላይ የወሠደውን እርምጃ እንዴት ይመለከቱታል? ለኛ ይሄ ነገር የተለየ እውቀት የሚጠይቅ አይደለም፡፡ ስቴት ካፒታሊዝም ወይም መንግስታዊ ከበርቴ የምትለው ስርአት አይነተኛ መገለጫው ነው፡፡ ነጋዴውን ህብረተሠብ የሚያሸማቅቅ፣ የመንግስትን ሚና የሚያጐለብት ነው፡፡ የንግዱን ማህበረሠብ የመንግስት ባለስልጣን ጥገኛም እንዲሆን ያደርገዋል፡፡ ጉዳዩን ለማስፈፀም፣ ስራውንም ለመስራት ሣይወድ በግዱ የመንግስት ባለስልጣናት አሽከር ይሆናል፡፡ ነጋዴውና የንግዱ ማህበረሠብ እየተዳከመ መንግስት እንዲተካው ነው ጥረት እየተደረገ ያለው፡፡ መጨረሻ ላይ ይህ ስርአት ወዴት ነው የሚሄደው? ሂደቱ የመንግስት ባለስልጣናትን ከበርቴ የሚያደርግ ነው፡፡

ምክንያቱም ነጋዴው ችግሮቹን የሚፈታበትን መንገድ የሚያመለክት አይደለም፡፡ ባለሃብቱ በጥርጣሬ ነው የሚታየው፡፡ ታማኝ አይደለም፣ ብቁ አይደለም፣ ስርአት የለውም እየተባለ ነው፡፡ ግለሠብ ነጋዴውን በጥርጣሬና በስጋት የማየት አዝማሚያ አለ፡፡ ስግብግብ፣ ሌባ፣ ወንበዴ ወዘተ--- ተደርጐ ነው የሚታየው፡፡ አሁን የተያዙት ባለስልጣኖች ይሄ ሁሉ ጉድ እያለባቸው ነው ነጋዴውን ሲያስፈራሩት፣ ሲዝቱበትና ኪራይ ሠብሣቢ ሲሉት የኖሩት፡፡ ስርአቱ ለእነዚህ ባለስልጣኖች መደራደሪያ በር ከፍቶላቸዋል፡፡ የፈለጉትን ነጋዴ በፈለጉት ጊዜ ጠርተው እያሸማቀቁና ስሙን እያጠፉ ህገወጥ በሆነ መንገድ መጠቀሚያ አድርገውታል፡፡ ይሄ ለኔ ሠዎችን የማሠርና ያለማሠር ጉዳይ ብቻ አይደለም፤ የስርአቱን የአስተሣሠብ ለውጥ የሚፈልግ ነው፡፡

የመንግስት ሹመኞችና ባለስልጣኖች የነጋዴውን ማህበረሠብ እንደ ሌባ፣ አታላይ፣ አጭበርባሪ፣ ኪራይ ሠብሣቢና ጠላት አድርገው የሚያዩበት ሁኔታ እስካልተለወጠ ድረስ ሙስናው ይቀጥላል፣ የመደራደሪያ በር ነው የሚከፍተው፡፡ አሁን የወሠዱት እርምጃ የሚደነቅ ነው፡፡ በሂደት ግን ውሣኔውንም የምናየው ይሆናል፡፡ አሁን የተደረገው “የበረዶ ጫፍ ነው” (Tip of the ice burg) እንደሚሉት ፈረንጆቹ፡፡ ትልቁ ጫፍ ገና ውሃው ውስጥ ነው ያለው፡፡ እንጀራ ጋግራ ከምትሸጥ ሴት ጀምሮ ገንዘብ የሚሠበሰብ መስሪያ ቤት፣ በዚህ ደረጃ መርከስና መበስበስ ውስጥ ከገባ፣ ሥርዓቱ ለአደጋ መጋለጡን ነው የሚያሳየው፡፡ በአጠቃላይ ስርአቱ የተጋረጠበት አደጋ መገለጫው ይሄ ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚህም በፊት ሙስና ነበረ፤ ግን በመቶ ሚሊዮኖች አልነበረም፡፡ ነጋዴው አቤት የሚልበት ነፃና ገለልተኛ አካል ነበረው፤ አሁን ግን መስሪያ ቤቱ የራሱ ፖሊስ አለው፡፡

ዳኛ ነው የፈለገውን ነገር ይፈርዳል፡፡ አቃቤ ህግ ነው፡፡ ታዲያ እንዴት ከዚህ መስሪያ ቤት ጋር መስራት ይቻላል? ይሄ እኮ ከመንግስትም በላይ ስልጣን የተሠጠው አካል ነው፡፡ እነዚህ ሠዎች ዳኛ ናቸው፣ ፍርድ ቤት ናቸው፣ አቃቤ ህግ ናቸው፣ ፖሊስ ናቸው፡፡ ስርአቱ እንደፈለጉ እንዲፈልጡ እንዲቆርጡ ስልጣን ስለሠጣቸው፣ የድፍረታቸው ድፍረት ቤታቸው በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ማስቀመጣቸው ተነግሮናል፡፡ ስርአቱን እንዳለ በገንዘብ፣ በጉቦ መቆጣጠር የሚችሉበት ደረጃ ላይ መድረሣቸውን ነው የሚያመለክተው፡፡ አንድ ሌባ የሠረቀውን ነገር ቤቱ የሚያስቀምጠው እኮ በጣም ደፋር ሲሆን ነው፡፡ ይህ እንግዲህ የስርአቱ መገለጫ ነው፡፡ የተወሠደውን እርምጃስ እንደ መልካም ጅማሮ ማየት ይቻላል? ልትወስደው ትችላለህ፡፡ ግን ዋናው ችግር ግለሠቦቹ ላይ አይደለም፤ ሥርዓቱ ላይ ነው፡፡ ማህበረሠቡ ሙስናን የሚፀየፍ ፣ የመንግስት ባለስልጣናት ደግሞ ተገቢውን ክፍያ እያገኙ ስራቸውን እንዲሠሩ ማድረግ ነው ጠቃሚው፡፡ ይሄን ሠውዬ ብታስረው ገና የእሡ ርዝራዦችና መሠሎቹ በየመስሪያ ቤቱ አሉ፡፡

ይሄ ነገር እኮ ሲባል የከረመ ጉዳይ ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩም አንድ እጄን ታስሬ እየሠራሁ ነው እስከማለት ደርሠው ነበር፡፡ ይሄ የሚያሣየው ምን ያህል ስር የሠደደ ችግር እንደሆነ ነው፡፡ ግለሠቦችን ማሠር ሙስናን ለመዋጋት አንድ መገለጫ ነው፤ ዋናው ነገር ግን የአስተሣሠብ ለውጥ ነው፡፡ ፍትሃዊ የሆነ የህግ ስርአት ሊበጅ ይገባል፡፡ ለአንድ መስሪያ ቤት የእግዚአብሔርን ያህል ጉልበት ተሠጥቶት እንዴት ሙስናን መዋጋት ይቻላል፡፡ ህገ ወጥ ነገር ለመስራት ሁሉም ነገር ተመቻችቶለታል፡፡ ይህ እያለ እንዴት ነው ሙስናን መታገል የሚቻለው፡፡ እርግጥ ስርአቱ በሽታውን ተረድቶ እርምጃ ለመውሠድ መነሣሣቱ የሚበረታታ ነው፡፡ ነገር ግን ጉዳዩ እየተጋነነ እየተወራ ነው፡፡ አንዳንድ ነጋዴዎችም እንዲበረግጉ እየተደረገ ነው፡፡

በዚህ ጉዳይ መንግስት ጥንቃቄ ሊያደርግ ይገባል፡፡ ሠዎቹ እንደየጥፋታቸው ፍትህ ፊት ቀርበው ተመጣጣኝ ቅጣት የሚያገኙበትን መንገድ መከተል ነው እንጂ ድራማ መስራት አይጠቅምም፡፡ ማጋነን፣ ነገሩን ከሚገባው በላይ መለጠጥ፣ ማህበረሠቡ በዚህ ጉዳይ የተዛባ መረጃ ኖሮት ያልተገባ ነገር እንዲናገር ማድረግ ተገቢ አይደለም፡፡ እነዚህ ነጋዴዎች ተገደው የገቡ ሊሆኑም ይችላሉ፡፡ ሌሎች ደንግጠውና በርግገው ሃገር ጥለው እንዲሄዱ የሚያደርግ መሆን የለበትም፡፡ እነዚህ ሠዎች አሁንም ገና ተጠርጣሪ ናቸው፡፡ ስርአት ባለው መንገድ ተይዘው የሚቀጡ ከሆነም መቀጣት አለባቸው፡፡ አሁን ግን የሚወራው ያለቀ ጉዳይ ተደርጐ ነው፡፡ ቀድሞ በፕሮፓጋንዳ ግለሠቦቹን ወንጀለኛ አድርጐ ደምድሞ፣ ፍርዱ ትርጉም እንዲያጣ ማድረግ አይገባም፡፡ እነዚህ ሠዎች እኮ በአንድ ጊዜ ስማቸው ወርዷል፣ የፕሮፓጋንዳው ሠለባ ሆነዋል፡፡ ሌሎችም እንዲበረግጉ ሆኗል፡፡ ነገር ግን መንግስት “እነዚህ ግለሠቦች ተይዘዋል፣ ሌላው ነጋዴ ተረጋግቶ ስራውን ይስራ” ማለት ነበረበት፡፡ ጠቅለል ብሎ ሲታይ የዚህ ሁሉ መሠረታዊ ችግር ይሄ መስሪያ ቤት የተሠጠው ከእግዚአብሔር ያልተናነሠ ስልጣን ነው፡፡ መንግስት አሁንም በነጋዴው ላይ ያለውን የተዛባ አመለካከት ይለውጥ፡፡

  • ክሳት የሚታይባቸው አቶ መላኩ፤ “ያለመከሰስ መብቴን ትቼዋለሁ” አሉ፡፡
  • “ፀሐይና ነፋስ በማይገባበት ክፍል ለብቻዬ ታስሬያለሁ” - አቶ መላኩ
  • “በስርዓቱ መሰረት ችግሮችን ለመፍታት እንጥራለን” - ማረሚያ ቤት
  • የተጠርጣሪዎች ቁጥር 31 ደርሷል፤ ሰኞ ፍ/ቤት ይቀርባሉ

የሚኒስትሮች ካቢኔ አባል የሆኑት የጉምሩክና ገቢዎች ባለሥልጣን ዋና ዳሬክተርና ምክትላቸውን ጨምሮ በሙስና ተጠርጥረው የታሰሩ ታዋቂ ባለሃብቶች ፍ/ቤት ሲቀርቡ የሰነበቱ ሲሆን፤ የፀረ ሙስና ኮሚሽን በሁለት ሳምንት ውስጥ ምርመራውን አጠናቅቆ ክስ እንዲመሰርት ፍ/ቤት አዘዘ፡፡ የዋስ መብት ያልተፈቀደላቸው ተጠርጣሪዎች፣ ከጠበቃ ጋር የመገናኘት መብታችን እንዲከበር ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ ቢሰጥም ማረሚያ ቤት ፈቃደኛ አልሆነም በማለት አማርረዋል፡፡ በሦስት የምርመራ መዝገብ ከፍሎ ተጠርጣሪዎችን ወደ ፍ/ቤት ያቀረበው የፀረ ሙስና ኮሚሽን፤ በአንደኛው መዝገብ ሰባት ተጠርጣሪዎችን አካትቷል፡፡

ከአሁን ቀደም አራጣ በማበደር፣ ታክስ በማጭበርበርና በኮንትሮባንድ ንግድ ከተከሰሱ ሰዎች ጉቦ ተቀብለው ክስ እንዲቋረጥ አድርገዋል በሚል ጭብጥ ዙሪያ የምርመራ መዝገብ የተከፈተባቸው የሚከተሉት ናቸው፡፡ አቶ መላኩ ፋንታ - የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ እሸቱ ወልደሰማያት - የባለስልጣኑ የአቃቤ ህግ ዳሬክተር አቶ መርክነህ አለማየሁ - የባለስልጣኑ የወንጀል መከላከል ቡድን መሪ አቶ አስመላሽ ወልደማርያም - የቃሊቲ ጉምሩክ ሃላፊ አቶ ከተማ ከበደ - የኬኬ ኩባንያ ባለቤት አቶ ስማቸው ከበደ - የኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ባለቤት ዶ/ር ፍቅሩ ማሩ - የህክምና ባለሙያ ሰባቱ ተጠርጣሪዎች ፍ/ቤት በቀረቡበት የምርመራ መዝገብ ከፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን ጋር ያደረጉት የቃል ክርክር፣ በዋስ መብትና መቼ ክስ መቅረብ አለበት በሚል ጥያቄ ዙሪያ ነው። አቶ መላኩ ፋንታ በጠበቃቸው በኩል ባቀረቡት መከራከሪያ፣ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል እንደሆኑ ጠቅሰዋል፡፡

የምክር ቤት አባል እጅ ከፍንጅ ካልተያዘ በቀር ያለመከሰስ መብቱ ሳይነሳ መታሰር የለበትም ብለዋል - የአቶ መላኩ ጠበቃ፡፡ መንግስት የሚያውቀው ህመም እንዳለባቸውና የህክምና ክትትል ሲደረግላቸው መቆየቱን አቶ መላኩ ጠቅሰው፤ ህክምናው በማረሚያ ቤት ሳይቋረጥ እንዲቀጥል ጠይቀዋል፡፡ ከቤተሰቦቻቸው፣ ከጠበቃቸው እና ከአማካሪያቸው ጋር ለመገናኘት እንዲፈቀድላቸው ያቀረቡት ጥያቄ፣ የሁሉም ተጠርጣሪዎች ጥያቄ ነው፡፡ ከጠበቃና ከቤተሰብ ጋር የመገናኘት መብታቸውን በሚመለከት ተጠርጣሪዎቹ አቤቱታ ያቀረቡት በመጀመሪያው እለት ነበር፡፡ ፍ/ቤቱም የተጠርጣሪዎችን ጥያቄ በመቀበል፤ የማረሚያ ቤት ኃላፊዎች የተጠርጣሪዎችን መብት እንዲያከብሩ በማሳሰብ ከወዳጅ ቤተሰብ ጋር እንዲገናኙ ማድረግ እንዳለባቸው ትዕዛዝ ሰጥቷል፡ የአካል ጉዳተኛ መሆናቸውን በመጥቀስ ልዩ ድጋፍና እንክብካቤ እንዲደረግላቸው አቶ መርክነህ ያቀረቡት አቤቱታ ላይ ግን ፍርድ ቤቱ የሰጠው ትዕዛዝ የለም፡፡

የአቶ መላኩ ያለመከሰስ መብትን በሚመለከት ደግሞ፣ ተጠርጣሪው የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ለአርብ እንዲያቀርቡ ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ ሰጥቶ ነበር፡፡ አርብ ዕለት የቀረቡት አቶ መላኩ የምክር ቤቱ አባል መሆናቸውን የሚያረጋግጥ ማስረጃ ካቀረቡ በኋላ ጓደኞቼ እንደሚሆኑት ለመሆን ያለመከሰስ መብቴን ላለመጠቀም ወስኛለሁ ብለዋል - አቶ መላኩ፡፡ የፀረ- ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን ወደ ፍ/ቤት ባቀረባቸው ተጠርጣሪዎች ላይ ክስ ለመመስረት ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ያስፈልገኛል በማለት ሲጠይቅ፣ ተጠርጣሪዎች ተቃውሟቸውን አሰምተዋል፡፡ የቤትና የቢሮ ብርበራ አካሂዶ ስለጨረሰና ምርመራ አጠናቅቄአለሁ ብሎ ስለተናገረ ተጨማሪ ቀን ሊፈቀድለት አይገባም ብለዋል - ተጠርጣሪዎች፡፡ መርማሪው ቡድን በበኩሉ፤ ክስ ለመመስረት በቂ ማስረጃ አሰባስቤያለሁ አልኩ እንጂ ምርመራ ጨርሻለሁ አላልኩም በማለት ምላሽ ሰጥቷል።

ፍ/ቤቱ የመርማሪውን ቡድን ጥያቄ በመቀበል፣ ከወንጀሉ አዲስነት፣ ውስብስብነትና ስፋት አንፃር 14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ፈቅጃለሁ ብሏል፡፡ በተመሳሳይ ክስ በሁለተኛው መዝገብ ሰኞ ከሰዓት ፍ/ቤት የቀረቡት የባለስልጣኑ ምክትል ዳሬክተር አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስን ጨምሮ አስራ አንድ ተጠርጣሪዎች ቢሆኑም፣ በፌደራል ፖሊስና ደህንነት ሃይሎች ክትትል በቁጥጥር ስር የዋሉት የባለስልጣኑ የወንጀል ምርመራ ዳሬክተር አቶ ተወልደ ብስራት 12ኛ ተጠርጣሪ ሆነው በማክሰኞ ችሎት ተካተዋል፡፡ በዚህ መዝገብ የተካተቱት ባለስልጣናትና ባለሃብቶች አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስን ጨምሮ አቶ በላቸው በየነ፣ አቶ ነጋ ገ/እግዚያብሄር፣ አቶ ምህረትአብ አሰፋ፣ አቶ ሙሴ ጋሻው፣ አቶ አሞኘ ታገሰ እንዲሁም የአቶ ገ/ዋህድ ባለቤት ኮ/ል ሃይማኖት ተስፋዬ ከነእህታቸው ወ/ሮ ንግስቲ ተስፋዬ ይገኙበታል - ወ/ሮ ንግስቲ ልጅ ሃብታሙ ገ/መድህን ጭምር፡፡ ከአንደኛ እስከ 8ኛ የተጠቀሱት ያልተፈቀደ ሲሚንቶ ወደ ሃገር ውስጥ እንዲገባ አድርገዋል የተባሉት ተጠርጣሪዎች፣ ካሁን ቀደም በኮንትሮባንድ ንግድ የተከሰሱ ሰዎችን ከክስ ነፃ እንዲሆኑ አድርገዋል ተብለዋል፡፡ ቀሪዎቹ ሦስት ታሳሪዎች የአቶ ገ/ዋህድ ባለቤትና ቤተሰብ ናቸው - ሰነድ በማሸሽና በመደበቅ የተጠረጠሩ፡፡

አቶ ገ/ዋህድ ለፍርድ ቤቱ ባቀረቡት የቃል ክርክር ላይ የመንግስት ሚዲያ ዘገባዎች ላይ ተቃውሞ አሰምተዋል፡፡ የተጠረጠርኩበት ጉዳይ በፍርድ ሂደቱ የሚጣራና እልባት የሚያገኝ ሆኖ ሳለ፣ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በየእለቱ ስሜን የሚያጎድፍ ዘገባ እያቀረበ ነው በማለት ዘገባዎቹ እንዲታገዱላቸው ቢጠይቁም፣ ፍርድ ቤቱ ያስተላለፈው ትዕዛዝ የለም፡፡ ባለቤቴ እና የቤተሰብ አባላት በመታሰራቸው ልጆቼ የት እንዳሉ አላውቅም ያሉት አቶ ገ/ዋህድ፤ ባለቤቴ የፈፀመችው ወንጀል የለም በማለት እንዲለቀቁላቸው ጠይቀዋል፡፡ ፍርድ ቤቱ ግን እሳቸው መከራከር የሚችሉት ለራሳቸው ብቻ መሆኑን በመግለፅ ጥያቄያቸውን ሳይቀበል ቀርቷል፡፡ ይሁንና የፀረ ሙስና ኮሚሽን መርማሪ ቡድን በኮ/ል ሃይማኖት ክስ ላይ አስተያየት እንዲሰጥበት ፍ/ቤት አዟል፡፡ የመርማሪ ቡድኑ በበኩሉ፤ ኮ/ል ሃይማኖት፣ ወ/ሮ ንግስቲ እና ልጃቸው ለምን እንደታሰሩ ለማስረዳት በሰጠው ምላሽ፣ የአቶ ገ/ዋህድ ሰነዶችን የማሸሽና የመደበቅ ድርጊት ፈጽመዋል ብሏል፡፡ በሙስና የተጠረጠረን ግለሰብ ሰነድ ማሸሽና መደበቅ ራሱ፣ በሙስና ክስ የሚታይ ነው ብሏል - መርማሪው ቡድን፡፡

ሁሉም ተጠርጣሪዎች የዋስትና መብታቸው ተጠብቆላቸው ከእስር እንዲለቀቁና ጉዳያቸውን በውጪ ሆነው እንዲከታተሉ የጠየቁ ቢሆንም፣ ፍርድ ቤት ጥያቄያቸውን ውድቅ በማድረግ ለመርማሪው ቡድን የ14 ቀናት ቀጠሮ ፈቅዷል፡፡ በሶስተኛው መዝገብ የናዝሬት ጉምሩክ ስራ አስኪያጅን ጨምሮ፣ ኮንትሮባንድ የማስገባትና የመተባበር ድርጊት ፈጽመዋል ተብለው የተጠረጠሩ መርማሪዎችና ባለሃብቶች 6 ናቸው፡፡ ስራ አስኪያጁ አቶ መሃመድ ኢሳ፣ ሰይፈ ንጉሴ፣ ዘሪሁን ዘውዴ፣ ማርሸት ተስፋዬ፣ ሙሉቀን ተስፋዬ እና ዳኜ ስንሻው ሰኞ እለት ፍርድ ቤት ከቀረቡ በኋላ፤ ከአማካሪ ጠበቆቻቸው ጋር ተወያይተውና ለቃል ክርክር ተዘጋጅተው እንዲመጡ ተነግሯቸው ነበር፡፡ ይሁንና ከጠበቆቻቸው ጋር እንዲገናኙ ስላልተፈቀደላቸው ማረሚያ ቤቱ በፍ/ቤት ትዕዛዝ መሰረት ተጠርጣሪዎች ከጠበቆቻቸው ጋር እንዲገናኙ መፍቀድ እንዳለበት ተገልፆለት እንደገና ለሐሙስ ግንቦት 9 ቀን የቃል ክርክሩ እንዲካሄድ ተቀጥሯል፡፡

ሁለተኛ መዝገብ የተከሰሱት በእነ አቶ ገ/ዋህድ ጉዳይም ማረሚያ ቤቱ ጠበቆች እንዲገቡ ባለመፍቀዱ፤ ተጠርጣሪዎች ከጠበቆቻቸው ጋር ሳይማከሩ ነበር ፍ/ቤት የቀረቡት፡፡ እዚያው ፍርድ ቤቱ ውስጥ ነው፣ ለ10 ደቂቃ ያህል ተመካክረው የቃል ክርክራቸውን እንዲቀጥሉ የተደረገው፡፡ ጠበቆች ከተጠርጣሪዎች ጋር እንዲገናኙ ፍርድ ቤት ያስተላለፈው ትዕዛዝ ለምን በማረሚያ ቤት ተፈፃሚ እንዳልተደረገ ኮማንደር አበበ ብርሃኔ ወደችሎት ቀርበው እንዲያሰረዱ ታዘዋል፡፡ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባልነት ማረጋገጫ ይዘው በመቅረብ ያለ መከሠስ መብታቸውን እንዲያስረዱ ለትናንት ተቀጥረው የነበሩት አቶ መላኩ ፈንታ፤ ትናንት ከሰዓት በኋላ ለተሰየመው ችሎት ማስረጃውን አቅርበዋል፡፡ የመክሳትና የመገርጣት ምልክት የሚታይባቸው አቶ መላኩ፤ ያለመከሠስ መብታቸውን መጠቀም እንደማይፈልጉ በመግለፅ ጉዳያቸው ከሌሎቹ ተጠርጣሪዎች ጋር እንዲታይ ፍርድ ቤቱን ጠይቀዋል፡፡

“ያለመከሰስ መብቴን ትቼዋለሁ፤ እንደ ጓደኞቼ እሆናለሁ” ብለዋል፡፡ የፀረ ሙስና መርማሪ ቡድን በበኩሉ፤ አቶ መላኩ በ2000 ዓ.ም ምርጫ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል እንዲሆኑ ቢመረጡም ዘንድሮ በሚያዝያ ወር በተካሄደው ምርጫ ስላልተመረጡ ያለመከሰስ መብት የላቸውም ብሎ ተከራክሯል፡፡ ፍ/ቤቱ የመርማሪውን ቡድን መከራከሪያ ባይቀበለውም፤ አቶ መላኩ በራሳቸው ፈቃድ ያለመከሰስ መብታቸውን በመተዋቸው ሂደቱ እንዲቀጥል ወስኗል፡፡ የአቶ መላኩ ጠበቃ ትናንት እንደገና ለፍርድ ቤቱ ባቀረቡት አቤቱታ፤ ደንበኛቸው በማረሚያ ቤት ጨለማ ቤት እንዲቀመጡ ከመደረጉም በላይ ምግብና መድሃኒት በአግባቡ እየቀረበላቸው አይደለም ብለዋል፡፡ ጠበቃው አክለውም፤ አቶ መላኩ ያጋጠማቸው የህመም አይነት ከኢትዮጵያ የህክምና ባለሙያዎች አቅም በላይ እንደሆነ በመንግስት የሚታወቅ በመሆኑ የተሻለ ህክምና የሚያገኙበት መንገድ እንዲመቻችላቸው ጠይቀዋል፡፡

ህክምናውን በቶሎ ካላገኙ ለህይወታቸው አስጊ መሆኑን በመግለጽ ጭምር፡፡ ሌላው በጠበቃው የቀረበው ቅሬታ ደንበኛቸው ከቤተሰቦቻቸው፣ ከልጆቻቸው እና ከባለቤታቸው እንዲሁም ከጠበቃቸው ጋር እንዳይገናኙ ተደርገዋል የሚል ነው፡፡ ተጠርጣሪዎች ከጠበቆች ጋር እንዲገናኙ በፍ/ቤት የተላለፈው ማሳሰቢያ ለምን ተፈፃሚ እንዳልሆነ ማረሚያ ቤቱ እንዲያስረዳ በመታዘዙ ኮማንደር ብርሃኑ አበበ ትናንት ፍ/ቤት ፊት ቀርበዋል፡፡ “ጠበቃው ደንበኛቸው በጨለማ ክፍል ተቀምጠዋል ያሉትን እቃወማለሁ በማረሚያ ቤቱ ጭለማ የሚባል ክፍል የለም” ያሉት ኮንደር ብርሃኑ፣ ጤናን በተመለከተ ማረሚያ ቤቱ ውስጥ ተጠርጣሪዎችን የሚያክም ክሊኒክ አለ፡፡ ከዚያ ካለፈም ስርአቱ በሚፈቅደው መሠረት ሌላ ቦታ ሊታከሙ ይችላሉ፡፡ እንደተባለው ሣይሆን መድሃኒት ተገዝቶላቸዉ ተጠቅመዋል” ብለዋል፡፡ “ከቤተሠብ ጥየቃ እንዲሁም ከጠበቆችና ደንበኞች ግንኙነት ጋር በተያያዘ ችግር ተፈጥሮብኛል ብሎ የጠየቀ የለም፣ እኛም አሠራሩ በሚፈቅደው መሠረት፤ ህገ መንግስቱ በሠጣቸው መብት ተጠቅመው እንዲገናኙ እንፈልጋለን” ብለዋል ኮማንደር ብርሃኑ፡፡ ተፈጠሩ የተባሉትን ችግሮች ለመቅረፍ እንደሚጥሩ ኮማንደር ብርሃኑ ለፍርድ ቤቱ ቃል ገብተዋል፡፡

አቶ መላኩ ፈንታ በበኩላቸው፤ ስርአቱ ትክክል ሆኖ ሣለ፣ የአፈፃፀም ችግር በማረሚያ ቤቱ እንዳጋጠማቸው ገልፀው፤ “የህክምና ጉዳይ ጠይቄያለሁ፡፡ መድሃኒቱ ውጪ ይገዛ ቢባልም በተባለው ቀን አይደለም የደረሠልኝ፡፡ የታሠርኩት ጭለማ ቤት ሳይሆን አንድ ክፍል ውስጥ ለብቻዬ ነው፡፡ ፀሃይና አየር አላገኝም፤ ለሽንት ብቻ እንድወጣ ይፈቀድልኛ” ብለዋል፡፡ ማረሚያ ቤቱ የቀረቡበትን ቅሬታዎች እንዲያስተካክል ትዕዛዝ ከተሰጠ በኋላ፤ ለግንቦት 19 ቀን ቀጠሮ እንደተያዘ ፍ/ቤቱ ገልጿል፡፡ በተመሣሣይ ከጠበቆቻቸዉ ጋር ተመካክረው እንዲቀርቡና የቃል ክርክራቸውን ትናንት እንዲያከናውኑ ተቀጥረው የነበሩት በእነ አቶ መሃመድ ኢሣ መዝገብ የተከሠሡት 6 ግለሠቦች፤ በማረሚያ ቤቱ ባለመቅረባቸው አቃቤ ህግ ሠኞ ግንቦት 12 ቀን 4ኛ መዝገብ ከሚከፈትባቸው ከእነ ዳዊት ኢትዮጵያ ጋር እንዲቀርቡ ፍ/ቤቱ ትዕዛዝ ሠጥቷል፡፡ ኮሚሽኑ በተጠርጣሪነት 7 ተጨማሪ ግለሠቦችን በቁጥጥር ስር ያዋለ ሲሆን፣ እነሡም አቶ ዳዊት ኢትዮጵያ፣ ፍፁም ገ/መድህን፣ ማሞ ኪሮስ፣ አለልኝ ተስፋዬ፣ አሸብር ተሠማ፣ ማሞ አብዲ መሆናቸው ታውቋል፡፡ ኮሚሽኑ በተጠርጣሪነት የያዛቸው ግለሠቦች ቁጥርም ከ25 ወደ 32 በማደጉ 4ኛ የምርመራ መዝገብ ይከፈታል ተብሏል፡፡

Published in ዜና
  • ኢህአዴግም እንደ ድርጅት ሙሰኛ ነው - ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ
  • ገቢዎች ከመንግስትም በላይ ስልጣን የተሰጠው አካል ነው - አቶ ሙሼ ሰሙ
  • ማጥመጃው ትላልቅ ዓሳዎችን ካጠመደ እንተባበራለን - ዶ/ር ያዕቆብ ኃ/ማርያም
  • የእርምጃውን አቅጣጫ ለማወቅ ቀጣዩን ማየት ያስፈልጋል - ዶ/ር መረራ ጉዲና

በፌዴራል የፀረ ሙስና ኮሚሽን በሙስና ተጠርጥረው የተያዙ ከፍተኛ ባለስልጣናት ጉዳይ ከፖለቲካ ጋር የተያያዘ እንዳይሆን ስጋት አለን የሚሉ ተቃዋሚዎች፤ እውነቱን የምናውቀው በእርምጃው ቀጣይነት ነው ብለዋል፡፡ መንግስት አላማው ሙስናን ማጥፋት ከሆነ ግን የሚደነቅና የሚበረታታ ተግባር ነው ሲሉ አወድሰዋል፡፡ አሁን የተወሠደው እርምጃ ግዙፉን የሙስና ችግር ዝም ብሎ መነካካት ነው ያሉት የመድረክ አመራር አባል ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ፤ አሁን ባለው ሁኔታ ኢህአዴግ እርምጃ መውሰድ ጀምሯል ማለት አይቻልም፤ አሁንም ትልልቅ አሳዎች አልተነኩም ብለዋል፡፡ በመላ ሃገሪቱ ሙስና መስፋፋቱን የሚናገሩት ፕ/ር በየነ፤ ራሱ ገዢው ፓርቲ የሚያንቀሣቅሣቸው የንግድ ድርጅቶች ከሙስና የፀዱ አይደሉም በማለት ተችተዋል፡፡

የኢዴፓ ሊቀመንበር አቶ ሙሼ ሠሙ በሙስና የተጠረጠሩ ባለስልጣኖችና ባለሃብቶች ለህግ እንዲቀርቡ መደረጉን ቢደግፉም ዋነኛ የችግሩ ምንጭ ግለሰቦች ሳይሆኑ ስርአቱ ነው ይላሉ፡፡ ስርአቱ ለእነዚህ ባለስልጣናት የመደራደርያ በር ስለከፈተላቸው የፈለጉትን ነጋዴ በፈለጉት ጊዜ ጠርተው እያሸማቀቁና ስሙን እያጠፉ በጠላትነት የሚያዩበት ሁኔታ ካልተቀየረ ሙስናን ማጥፋት አይቻልም ብለዋል፡፡ ተጠርጣሪዎቹን ማሰር ሙስናን የመዋጋት አካል መሆኑን ጠቁመው፤ ዋናው ግን የአስተሳሰብ ለውጥ ነው ባይ ናቸው - አቶ ሙሼ፡፡ የቀድሞው የቅንጅት አመራር አባልና አለማቀፍ የህግ ምሁሩ ዶ/ር ያዕቆብ ሃ/ማርያም በሰጡት አስተያየት፤ እርምጃው የሚቀጥል ከሆነ የሚመሠገን ነው፤ ካልሆነ ግን በፖለቲካ ግጭት ምክንያት የተፈጠረ ያስመስለዋል ብለዋል፡፡

“ከተያዙት የበለጡ ትላልቅ አሳዎች መኖራቸውም መዘንጋት የለበትም ሲሉም አሳስበዋል፡፡ በሙስና ተጠርጥረው የተያዙት ሠዎች ጉዳይ ፖለቲካዊ ይመስላል ያሉት የመኢአድ ፕሬዚዳንት ኢ/ር ሃይሉ ሻውል፤ የተያዙት በእርግጥም በሙስና የተጠረጠሩበት ጉዳይ እውነት ከሆነ ግን እርምጃው ቀጣይ እንደሚሆን አምናለሁ ብለዋል፡፡ የመድረክ አባል የሆኑት ዶ/ር መራራ ጉዲናም እርምጃውን በጥርጣሬ ነው የሚመለከቱት፡፡ የእርምጃውን አቅጣጫ ለማወቅ ቀጣዩን ሂደት ማየት ያስፈልጋል ይላሉ - ዶ/ር መረራ፡፡ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ የሙስናን ጉዳይ በግሌ እከታተላለሁ ማለታቸውን ያስታወሱት ዶ/ር መረራ፤ ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊም “አንድ እጃችንን በመንግስትና በግል ሌቦች ታስረን ነው የምንሰራው” እያሉ ለውጥ ሳያመጡ ነው ያረፉት በማለት “ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያምስ አቅም አላቸው ወይ?” ሲሉ ጠይቀዋል፡፡

ፀረ ሙስና ኮሚሽን እስካሁን ብቃት አልነበረውም፤ አሁንም ሁለት ባለስልጣናትን ስላሰረ ብቃት አለው ብሎ ለመደምደም ያስቸግራል ብለዋልም፡፡ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዲኤታ አቶ ሽመልስ ከማል በበኩላቸው፤ የተወሠደው እርምጃ መላውን ህብረተሠብ ያግባባና የህዝቡ ፖለቲካዊ ድጋፍ የታየበት ነው በማለት እርምጃውን ከፖለቲካ ጋር የሚያገናኙ ወገኖችን ኮንነዋል፡፡ እነዚህ ወገኖች የህብረተሠቡንና የመንግስትን ጥረት የማክሸፍና የማምከን ሙከራ እያደረጉ ነው ያሉት አቶ ሽመልስ፤ ይህን አይነቱን እርምጃ ፖለቲካዊ ነው ማለት ለኪራይ ሠብሣቢነት አሠራር ድጋፍ መስጠት ነው ብለዋል፡፡ የፌደራል የፀረ ሙስና ኮሚሽን የሥነምግባር ትምህርት ዳሬክተር አቶ ብርሃኑ፤ ኮሚሽኑ ግንዱን ትቶ ቅርንጫፉ ላይ አተኩሯል የሚለውን አስተያየት አይቀበሉም፡፡ ከ“ሚኒስትር በላይ ግንድ ካለ ይንገሩን” ሲሉ ይሟገታሉ - ዳሬክተሩ፡፡ በሙስና የተጠረጠሩ ባለስልጣናትን ለመያዝ የማንንም ፈቃድ እንደማይፈልጉ ሲያስረዱም፤ እስካሁን በነፃነት እየሰሩ እንደሆነና በምርመራቸው ጣልቃ የገባባቸዉ እንደሌለ ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ ገልፀዋል፡፡

Published in ዜና

ከሦስት መቶ በላይ መኪኖች በጉምሩክ ተይዘው ያለ ስራ ለሁለት አመታት እንደተቀመጡ የገለፁ አስጐብኚ ድርጅቶች፣ የገቢዎችና የጉምሩክ ባለስልጣን ሃላፊዎች አቤቱታችንን ለመስማትም ሆነ እኛን ለማነጋገር ፍቃደኛ ባለመሆናቸው እንግልት ደርሶብናል ሲሉ ባካሄዱት ስብሰባ ገለፁ። በመቶ የሚቆጠሩ ድርጅቶች በአባልነት የያዘው የአስጐብኚዎች ማህበር ትናንት በጠራው አስቸኳይ ስብሰባ፣ የፀረ ሙስና ኮሚሽን እንቅስቃሴን እንደሚደግፍ በመግለፅ፣ የኛ አቤቱታና መረጃ ለኮሚሽኑ ጠቃሚ ግብአት ይሆናል ብሏል፡፡ የማህበሩ አባላት የሆኑ አስጐብኚ ድርጅቶች ከባለስልጣኑ መስሪያ ቤት ሃላፊዎች ከባድ ተጽእኖና እንግልት እንደደረሰባቸው ማህበሩ ገልፆ፤ ፀረ ሙስና ኮሚሽን የነሱን መረጃ የሚቀበል ዴስክ እንዲያቋቁም ጠይቀዋል፡፡

ለቱሪዝም እድገት የትራንስፎርሜሽን ኤጀንሲ እንዲቋቋም ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ መወሰናቸውን እንደሚደግፉ የገለፁ የማህበሩ አባላት፣ ካለፉት አራት አመታት ወዲህ ግን የቱሪዝም ዘርፉን በሚያቀጭጩ እንግልቶች ሳቢያ በርካታ አስጐብኚ ድርጅቶች እየተዳከሙና እየከሰሩ ከስራው ወጥተዋል ብለዋል፡፡ አስጐብኚ ድርጅቶች የቱሪዝም ስራቸውን ለማሳደግ ከውጭ ያስመጧቸው ከ300 በላይ መኪኖች ለሁለት አመታት ያለምንም ምክንያት ያለስራ በጉምሩክ ግቢ ውስጥ መቆማቸውን የማህበሩ አባላት ገልፀው፤ ሃላፊዎች ዘንድ ብንሄድም መፍትሔ አላገኘንም። የሚያንገላቱና የሚያንጓጥጡ ሃላፊዎች በርካታ በደሎችን ፈጽመውብናል ያሉት የማህበሩ አባላት፣ ይህንን በግልጽ የሚያሳዩ ማስረጃዎቻችን የፀረሙስና ኮሚሽን እንደሚቀበለን ተስፋ እናደርጋለን ብለዋል።

Published in ዜና

ጠ/ሚ ኃ/ማርያም በአስረጂነት ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ እንጠይቃለን ብለዋል

በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በአማራ ተወላጆች ላይ በደረሰው መፈናቀል ተጐጂዎች ፍትህ እንዲያገኙ መኢአድና ሰማያዊ ፓርቲ ክስ ሊመሰርቱ ነው፡፡ ጠ/ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በአስረጂነት ፍ/ቤት እንደሚቀርቡ ተጠቁሟል፡፡ የመኢአድ ፕሬዚዳንት ኢ/ር ሃይሉ ሻውል እና አለማቀፍ የህግ ባለሙያው ዶ/ር ያዕቆብ ሃ/ማርያም ከትላንት በስቲያ በጋራ በሠጡት መግለጫ፤ መረጃዎች ከተሰባሰቡና ከተደራጁ በኋላ በፌደራሉ ፍ/ቤት ወይም በክልሉ ፍ/ቤት ሁለት ዓይነት ክሶች እንደሚመሰረቱ ተናግረዋል፡፡ ክሱ የሚመሠረተው በዋናነት የዜጐች ከቦታ ቦታ የመዘዋወርና የመኖር መብት የሚደነግገውን የህገመንግስቱን አንቀጽ መነሻ በማድረግ ሲሆን በወንጀል እና በፍትሃብሔር ተከፋፍሎ ይቀርባል ተብሏል፡፡

በወንጀል ክሱ ላይ በተለይ ከዘር ማጥፋት ጋር የተያያዙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች እንደሚካተቱ የገለፁት ዶ/ር ያዕቆብ፤ ከተበዳዮች ከሚሰባሰቡት መረጃዎች በተጨማሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ከዚህ ቀደም ፓርላማ ቀርበው በክልሉ ዜጐች መፈናቀላቸውንና ችግሩን የፈጠሩት ኪራይ ሰብሳቢዎች መሆኑን በይፋ በመግለፃቸው ሌላ ማስረጃ ሳያስፈልግ ራሳቸው ፍርድ ቤት ቀርበው አስረጂ ይሆናሉ ብለዋል - ዶ/ር ያዕቆብ ሃ/ማርያም፡፡ ወንጀሉ በሰው ዘር ላይ ከተፈፀሙ ከባድ ወንጀሎች ተርታ የሚመደብ መሆኑን ያመለከቱት የህግ ባለሙያው፤ በኢትዮጵያ የወንጀለኛ መቅጫ ህግ ላይ ድርጊቱን የፈፀሙ እስከሞት ቅጣት ሊቀጡ የሚችሉበት ሁኔታ መቀመጡን ገልፀዋል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ የሚቀርበው የፍትሃብሔር ክስም በዋናነት ለወደመው ንብረትና ለደረሰው ሰብአዊ ቀውስ ካሣ የሚያስገኝ እንደሚሆን ተጠቁሟል፡፡

የክሱ አካሄድ በሃገሪቱ ያልተለመደ መሆኑን የገለፁት ዶ/ር ያዕቆብ፤ በአንድ ሰው ከሣሽነት ሌሎች ተመሳሳይ በደል የደረሰባቸው ወገኖች ፍትህ የሚያገኙበት አይነት ክስ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ክሱ ከሚመሠረትባቸው የመንግስት አካላት መካከል የፌዴራል ጉዳዮች ሃላፊዎች፣ የፖሊስ አባላት እንዲሁም የክልሉና የወረዳው ሃላፊዎች ዋናዎቹ እንደሚሆኑ ተገልጿል፡፡ ክሱን መቼና እንዴት ይጀመር የሚለውን ገና ጉዳዩ እየመከርንበት ነው ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤ በመጀመሪያ የተበደሉ ሰዎችን ውክልና ማግኘት እንደሚጠበቅባቸውና ከዚያም መረጃዎችን አሰባስበው በሁለት የህግ ባለሙያዎች በመታገዝ ክሱን እንደሚመሰርቱ ተናግረዋል፡፡

ከክሱ ምን ትጠብቃላችሁ ተብለው ለተጠየቁት ሲመልሱም፤ ውጤቱ ምን ይሆናል የሚለው በሂደት የሚታይ ጉዳይ መሆኑን የተናገሩት ባለሙያው፤ ክሱ ተቀባይነት ካጣ ወደ አለማቀፍ ፍርድ ቤት እንደሚያመሩ ዓለምአቀፍ የህግ ባለሙያው ገልፀዋል፡፡ በአማራ ተወላጆች ላይ በደቡብ ክልል በቤንቺ ማጅ ጉራፋርዳ አካባቢ እየደረሰ ያለው መፈናቀልና የሰብአዊ መብት ጥሰት ዛሬም አለመቆሙን ያስታወሱት የመኢአድ ፕሬዚዳንት ኢ/ር ሃይሉ ሻውል በበኩላቸው፤ በሀገሪቱ ዘረኝነት እየተስፋፋ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ መላው የኢትዮጵያ ህዝብ የዚህ ድርጊት ተባባሪ እንዳይሆንም ጥሪ አቅርበዋል - ኢንጂነሩ፡፡

Published in ዜና

በግል ባለሀብቷ በወ/ሮ አማረች ዘለቀ በ200 ሚሊዮን ብር የተሠራው ባለ 5 ኮከብ ሆቴል ዛሬ ይመረቃል፡፡ ዘመናዊው ሴንትራል ሐዋሳ ሆቴል ባለ መንታ ሕንፃ ሲሆን 70 የመኝታ ክፍሎች፣ ከ40 እስከ 1ሺ ሰዎች መያዝ የሚችሉ ሰባት የመሰብሰቢያ አዳራሾች አሉት፡፡ የመዋኛ ገንዳ፣ የወንዶችና የሴቶች ስፓ፣ የወንዶችና የሴቶች የውበት ሳሎን፣ ፑል ባር፣ ናይት ክለብ፣ አካባቢው እየቃኙ የሚዝናኑበት ቴራስ ባር፣ ጂምናዚየም ሬስቶራንት፣ ኮኒ ባር እንዲሁም ጊዜያዊ የእንግዶች ማረፊያ እንዳለውም ታውቋል፡፡

በምድር ቤቱ የመኪና ማቆሚያ ያለው ሆቴሉ፤ የንጽህና መስጫ ላውንደሪ፣ የባንክ አገልግሎትና የጉዞ ወኪል ቢሮዎችን በማሟላት ባለ 5 ኮከብ የሚያሰኘውን ደረጃ የያዘ መሆኑን ባለቤቷ ገልፀዋል፡፡ የሆቴሉ ግንባታ በሦስት ዓመት በመጠናቀቁ የከተማው አስተዳደር “የጊዜ ገደቡን በተገቢው መንገድ የተጠቀመ ኢንቨስትመንት” ሲል አወድሶታል፡፡ ከትንሽ ደረጃ ተነስተው የትልቅ ኢንቨስትመንት ባለቤት ለመሆን የበቁት ወ/ሮ አማረች ዘለቀ፤ ጽናት በተመላበት ብርታታቸው ለሴቶች ትልቅ አርአያ ሆነዋል ተብሏል፡፡ ሆቴሉ ለ250 ዜጐች የሥራ ዕድል መፍጠሩ ታውቋል፡፡

Published in ዜና

በሶሪያ መላ የታጣለትን የእርስበርስ ጦርነት በመሸሽ ወደ ዮርዳኖስ የተሰደዱ እናቶች፣ ህይወት ፈተና ሆኖባቸው ሴት ልጆቻቸውን “ለጊዜያዊ ትዳር” እየሸጡ ነው፡፡ ስደተኛ ወላጆች በሴት ልጆቻቸው ላይ መጨከን እንደጀመሩ የዘገበው ሲኤስ፣ ኑሮን ለመግፋት የሚያስችላቸው ብቸኛ አማራጭ ሆኖ ያገኙት ሴት ልጆቻቸውን በሺዎች በሚቆጠሩ ዶላሮች ለጋብቻ መሸጥ ነው፡፡ ከዮርዳኖስም ሆነ በሌሎች የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ጋብቻ ፈላጊ ወንዶች ለሴቷ ቤተሰቦች ገንዘብ የሚሰጡበት ባህል አለ፡፡ ይሄም ሆኖ ግን የሰሞኑ የዮርዳኖስ ስደተኛ ካምፖች “የጋብቻ ገበያ”፣ እርግጥም ወንዶች ሴቶችን ለዘላቂ ትዳር የሚገዙበት አይደለም፡፡ አብዛኛዎቹ “ትዳሮች” ከሳምንታት የዘለቀ ዕድሜ እንደማይኖራቸው የገለፀው ዘገባው፤ ይልቁንም “የወሲብ ገበያ” ሊባል የሚችል መሆኑን አስረድቷል፡፡

ይህንን የሴት ልጆች ሽያጭ ከሚያቀላጥፉትና ራሳቸውን “የጋብቻ ደላላ” ብለው ከሚጠሩት መካከል ሶሪያዊቷ ስደተኛ ኡም ማጄጅ አንዷ ናት፡፡ ኡም ማጄድ ከሰሞኑ እየጦፈ በመጣው የስደተኛ ልጃገረዶች ሽያጭ ገበያ ፋታ አጥታለች፡፡ የሞባይል ስልኳ በገዢዎች ጥሪ ተጨናንቋል፡፡ ኡም ማጄድ ከወላጆች ጋር በመነጋገር ለሽያጭ ከምታቀርባቸው ሴቶች ጠቀም ያለ ኮሚሽን ታገኛለች፡፡ ክብረ ንጽህናዋ ያልተገረሰሰ ልጃገረድ በሰሞኑ ገበያ እስከ 5ሺህ ዶላር ታወጣለች፡፡ አያ የተባለችዋ የ17 አመቷ ሶሪያዊት ስደተኛ አያ፤ ከቤተሰቦቿ ጋር በስደት ወደ ዮርዳኖስ ከመጣች አንድ አመት ያህል ሆኗታል፡፡

ይሄም ሆኖ ግን የስደት ኑሮ ለእሷም ሆነ ለቤተሰቧ አሳር ሲሆንባቸው፣ ብቸኛውን አማራጭ ለመውሰድ ተገደዱ፡፡ አያ ለ70 አመት ሳኡዲ አረቢያዊ “ትዳር ፈላጊ” ሽማግሌ በ3ሺህ 500 ዶላር ተሸጠች፡፡ ትዳር ፈላጊው ሽማግሌ ግን ከሙሽሪት አያ ጋር የመሰረተውን ትዳር ለማፍረስ የፈጀበት የአንድ ወር ጊዜ ብቻ ነበር፡፡ “ከእሱ ጋር ያሳለፍኩት አንድ አመት ልክ እንደ አስፈሪ ቅዠት ነበር፡፡ ግማሹን ወር በመራር ለቅሶ ነው ያሳለፍኩት፡፡ ከቤተሰቦቼ ጋር እንድገናኝና እንዳወራ አይፈቅድልኝም ነበር፡፡ ምርጫ አልነበረኝምና በሰቀቀን ነበር የምኖረው” ብላለች - አያ ስለ ሽያጩ ትዳሯ ስትናገር፡፡

እንዲህ ለጋ ልጃገረዶችን ለገበያ አቅርባ የምታሻሽጠው ኡም ማጄድ እየሰራችው ስላለችው ነገር ሃፍረትም ሆነ ፀፀት አይሰማትም፡፡ “መኖር የምችልበት ብቸኛው መንገድ ይህ “ስራ” ነው፡፡ ሶሪያውያን ስደተኞች በዮርዳኖስ ሌላ ስራ መስራትና ገቢ ማግኘት አንችልም፡፡ ስለዚህ ምን ማድረግ እንችላለን?...እንስረቅ?...እንግደል?” ትላለች ማጄድ፡፡ የሚገርመው ግን “አንቺስ የ13 አመት ልጃገረድ ልጅሽን ለመሸጥ ትፈቅጃለሽ?” ለሚለው የጋዜጠኞች ጥያቄ የሰጠችው መልስ ነው፡፡ “በፍፁም አላደርገውም!... ልጆቼን ከምሸጥ አይኖቼን አውጥቼ ብሸጣቸው እመርጣለሁ!” ነው ያለችው ማጄድ፡፡

Published in ዜና
Page 7 of 14