ሰማያዊ ፓርቲ ሠሞኑን በሠጠው መግለጫ፤ ከግንቦት 17 ጀምሮ መንግስት አልመለሳቸውም ባላቸው አራት ጉዳዮች ጋር በተያያዘ ሠላማዊ ሠልፍ እንደሚያካሂድ አስታውቋል፡፡ ሠልፉ የሚካሄደው የአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት የምስረታ ክብረ በዓል በሚካሄድበት ጊዜና ቦታ እንደሆነም ተገልጿል፡፡ በተጠራው ሠላማዊ ሠልፍና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከሠማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ከአቶ ይልቃል ጌትነት ጋር ያደረገችው ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡ ሠላማዊ ሠልፍ ማድረግ መብት ቢሆንም እስከዛሬ እየተጠሩ ሳይካሄዱ የቀሩ ሠልፎች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ በቅርቡም ከግራዚያኒ ሀውልት መቆም ጋር ተያይዞ ያደረጋችሁት የተቃውሞ ሰልፍ አልተሳካም፡፡ እንደውም የሰልፉ መሪዎች ታስረው ነበር፡፡ አሁንስ የሚሳካላችሁ ይመስላችኋል? እንግዲህ እኛ ትግል ሥናደርግ መሠረታዊ መነሻችን መርሁ ነው፡፡ ሁለተኛ ህጉ ነው። በእነዚህ ሁለት ነገሮች ነው የምንመራው።

በሌላ በኩል ሠው በመሆናችን መሠረታዊ መብት አለን። ሀሣባችንን በነፃነት የመግለፅ መብታችንም በህጉ ተደንግጓል፡፡ ሥለዚህ ህገ-ወጦች የሚያደርጉትን ማስፈራራትና ዛቻ አይተን መብታችንን ከመጠየቅ ወደ ኋላ አንልም፡፡ ወደ ፖለቲካ ትግል የገባንበት ዋናው ነገር፣ ህገ ወጥ አሠራርን በመንቀፍና በመቃወም ህጋዊ ስርዓት እንዲመጣ ህዝብን እየመራን ለመታገል ነው፤ አላማችንም ይሄው ነው፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ ህገ-ወጥ ነገር ሲያደርግ ያንን ታግለን መቀየር እንጂ እሱ ስለማይፈቅድ ብለን መብታችንን አሣልፈን መስጠት የለብንም፡፡ እንደውም አለመፍቀዱ ነው የበለጠ እንድንታገል የሚያነሣሣን፡፡ ኢህአዴግ የሚሰራውን ህገ ወጥ ድርጊት በመታገል ህጋዊ አሠራር ለማስፈን እንጥራለን፡፡ ኢትዮጵያ የታሪክ፣ የነፃነት ተምሣሌት የሆነ፣ መንግስት የነበራት አገር እንደመሆኗ፤ እንዲህ አይነቱን ችግር በዚህ ጊዜና ዘመን ማስተናገድ እጅግ ነውር ስለሆነ ይህን ለማስተካከል ነው እንደ አማራጭ ሀይል ተደራጅተን ትግል የጀመርነው፡፡

ስለዚህ ምንም ጥርጥር የለውም እናደርገዋለን፡፡ እንደባለፈው አይነት እስርና መስተጓጐል አይገጥመን ብላችሁ ታስባላችሁ?

እኛ እንግዲህ እሱን አናውቅም፡፡ እኛ መብታችን ነው፤ ኢህአዴግ ወንበዴ ሆኖ ካሠረን ግን አንቺም መጠየቅ ያለብሽ እሱን ነው፡፡ እኔን መጠየቅ ያለብሽ ህገ-ወጥ ናችሁ ካልሽ ብቻ ነው፡፡ እኔ ህጋዊ ከሆንኩና የምጠይቀውም መብቴን ከሆነ፣ ያንን ህግ የሚጥሠውንና የህዝብን ሥልጣን ይዞ ያለአግባብ ሌላውን የሚበድለውን አካል ነው “ለምን እንዲህ ታደርጋለህ” ብለሽ መጠየቅ ያለብሽ፡፡ እኔ የሚገርመኝ ሚዲያዎች ለምን እንዲህ ዓይነት ጥያቄ እንደምትጠይቁን ነው፡፡ ምክንያቱም መብታችን እንደሆነ ታውቃላችሁ። ነገር ግን ለኢህአዴግ ጉልበተኝነት መብት ሠጥታችሁታል፡፡ ጥያቄዬን ግልፅ ላድርግልዎት፣ መብት የላችሁም ማድረግ አትችሉም እያልኩ አይደለም፤ ነገር ግን በቅርቡ የጠራችሁት ሠላማዊ ሠልፍ ተበትኗል፤ እናንተም ታስራችሁ ነበር፡፡

አሁንስ ከዚያ የተለየ በምን መልክ ልታካሂዱት አስባችኋል ማለቴ ነው…? እኔ እነዚህ ነገሮች የሚፈቱት በትግል ነው ባይ ነኝ፡፡ አንድ አምባገነን ፈቅዶ የሚሠጠው መብት አለ ብዬ አላስብም፡፡ በአለምም ታሪክ አምባገነን ለዜጐች ዴሞክራሲን ወዶና ፈቅዶ ሠጥቶ አያውቅም፡፡ ህዝብ በታሪኩ ለዘላለም ተሸንፎ የቀረበት አጋጣሚ የለም፡፡ ነገር ግን ይህ የጊዜ ጉዳይ ነው፡፡ የተከለከሉ መብቶቻችንን ማረጋገጥ የምንችለው በትግል ነው፡፡ መብታችንን ማስከበር የምንችለው ትግሉን አጠንክረን ስንቀጥል እንጂ እጅ አጣጥፈን በመቀመጥ አይደለም፡፡ ለሠላማዊ ሠልፉ መነሻ ያደረጋችኋቸው አራት ነጥቦች የቆዩ ናቸው፡፡ ከዚህ አንፃር ሠልፉን ከአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት የምስረታ በዓል አከባበር ጋር ያደረጋችሁበት ምክንያት ምንድን ነው? ቀኑን ለምን መረጣችሁት?

ይህን የበዓል አከባበር የመረጥንበት ዋናው ነገር ወቅቱ ዓለም በሙሉ ወደ ኢትዮጵያ የሚያይበት ስለሆነ ነው፡፡ ያኔ የአገር ውስጥም ሆነ የውጭ ሚዲያዎች ለጉዳዩ ትኩረት የሚሠጡበት በመሆኑ እኛም በዚህን ወቅት ሠላማዊ ሠልፍ ማድረጋችን ድምፃችን ጐልቶና ከፍ ብሎ እንዲሠማልን ለማድረግ ብለን ነው፡፡ ይሄ ደግሞ የተለመደ ነው፡፡ በሌላውም ዓለም ትላልቅ ሥብሠባዎች በሚካሄዱበት ጊዜ እንዲሁ ድምፃቸውን ለማሰማት ሠልፍ ያደርጋሉ፡፡ ትኩረት ለመሣብ ነው? አቴንሽን ለመሣብ አይደለም (በቁጣ) ድምፅ ለማግኘት ነው፡፡ ትኩረት ለመሣብ የሚለው ቃል የእኛን ሀሣብ ያዛባዋል፡፡ ሠላማዊ ሠልፍ እንዳልኩሽ መብታችን ነው፡፡ ይሄንን መብታችንን ከህዝብ የምንጋራበትና ውጤታማ የምንሆንበት ጊዜ ነው፡፡ ለምሣሌ ኤርትራዊያን ኢትዮጵያ ውስጥ ሠላማዊ ሠልፍ ያደርጋሉ፤ የተለያዩ ስብሠባዎች በሚካሄዱበት ወቅት፡፡ የመንግስት ሚዲያም ለጉዳዩ ሽፋን ይሠጣል፡፡ ይሄ መንግስት ለኤርትራውያን ሠልፍ ከፈቀደና፣ ግብር ከፋይ ለሆኑት ኢትዮጵያዊያንና በህጋዊ መንገድ እውቅና ለተሠጠን ፓርቲዎች የማይፈቅድ ከሆነ፣ ከኢትዮጵያዊያን በላይ ለኤርትራዊያን ይጨነቃል ያዳላል ማለት ነው፡፡ ሠላማዊ ሠልፉ የተጠራባቸው የኑሮ ውድነት፣ መፈናቀል፣ እስራትና የሀይማኖት ጉዳዮች የኢትዮጵያን መንግስት የሚመለከቱ ናቸው፡፡ ለአፍሪካ ህብረት ተሠብሣቢዎች መናገሩ ለምን አስፈለገ? የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ በተጨማሪም ሠማያዊ ፓርቲ አዲስ እንደመሆኑ በዚህ አጋጣሚ ራሱን ፕሮሞት ለማድረግ ሥለፈለገ እንጂ ሠላማዊ ሠልፉ ይሳካልኛል ብሎ አይደለም ይባላል፡፡

የእርስዎ ምላሽ ምንድነው? በመሠረቱ አስተያየት መስጠት መብት ነው፡፡ በምናደርጋቸው እንቅስቃሴዎችና ስራዎች ሠዎች አስተያየት መስጠት፣ መተቸት መብታቸው ነው፡፡ በዚህ ተቃውሞ የለኝም። ነገር ግን ፓርቲው ራሱን ለማስተዋወቅ ነው የሚለውን አልቀበልም፡፡ ምክንያቱም እስካሁን በአገሪቱ ውስጥም ሆነ በአለም ላይ ስለ ሠማያዊ ፓርቲ ያልዘገበ የለም፡፡ ሠማያዊ ፓርቲ፤ በዚህ አስቸጋሪና የፖለቲካ ደብዛው በጠፋበት ጊዜ መጥቶ፣ በዓለም አቀፍ ማህበረሠብም ሆነ በኢትዮጵያዊያን ዘንድ አንድ የፖለቲካ ሀይል ሆኖ በመውጣት በኩል የተሣካለት ፓርቲ ነው፡፡ ራስን ለማስተዋወቅ የሠላማዊ ሠልፍን ስልት አንጠቀምም፡፡ ምክንያቱም ከበቂ በላይ የታወቅን ፓርቲ ነን፡፡ አሁን ጐግል ውስጥ ገብተሽ ሠማያዊ ፓርቲ ብትይ ታገኝናለሽ፡፡ እኛ ከምንለውም በላይ የታወቀ ፓርቲ ነው፡፡ ታወቅን የምትሉበት ምክንያት ምንድን ነው? ስለ ሠራን ይመስለኛል፡፡ ፖለቲካ ማለት የመርህ ትንተና ማለት አይደለም፡፡

አካዳሚ ስራም አይደለም፡፡ ለተጨባጭ ችግሮች ተጨባጭ መፍትሄ ማምጣት ነው፡፡ ስለዚህ ሠማያዊ ፓርቲ በአደረጃጀቱም በአመራር ብቃት፣ የህዝብ አጀንዳዎች ይዞ በመነሣት በኩል ያለው ተሠሚነትም ለትግሉ ያለውን ቆራጥነት የሚያሣይ ነው፡፡ ጉዳዩ የመንግስት ነው፤ በአፍሪካ ህብረት የስብሰባ ቀን ለምን ለተባለው እስከዛሬ የመንግስት ጉዳይ ነው ብለን ችግሮቹ እንዲስተካከሉ በተደጋጋሚ ብንጠይቅም ምላሽ አልተገኘም። አሁንም የኑሮ ውድነት አለ፣ አሁንም ዜጐች ይፈናቀላሉ፡፡ አሁንም ፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች በሽብርተኝነት ስም ወህኒ ነው ያሉት፣ አሁን መንግስት በሀይማኖት ጣልቃ ገብነት የሀይማኖት ሥርዓታችን ይከበር ባሉት ሙስሊሞች ላይ እስርና እንግልቱን አላቆመም፡፡ ስለዚህ በህብረቱ በኩል ጫና ለመፍጠርና ችግሮች የሚፈቱበትን መንገድ ለማፈላለግ ነው ሠልፉ ከህብረቱ 50ኛ ዓመት የምስረታ በዓል አከባበር ጋር እንዲገናኝ ያደረግንበት ምክንያት፡፡ ሠልፉ ተፈቀደና ተሣካ እንበል፡፡ ከዚያም የታሣሪ ቤተሠብ አለ፣ የሀይማኖቱ፣ የመፈናቀሉ፣ እንዲሁም የኑሮ ውድነቱ አንገፍግፎኛል የሚል ህዝብ ግልብጥ ብሎ ወጥቶ አገሩን ቢያጥለቀልቅ ሀላፊነቱን ትወስዳላችሁ፣ በምንስ ነው የምትቆጣጠሩት? የእኛ ፍላጐት ከላይ አንቺ እንደ ስጋት ያነሣሽው ነገር እንዲከሠትና ህዝቡ ግልብጥ ብሎ እንዲወጣ ነው የምንፈልገው፡፡

ህዝቡ ግልብጥ ብሎ ሲወጣ ደግሞ ይህንን የሚያረጋጋ ደሞዝ የሚከፈለው ደህንነትና ፖሊስ አለ። መጨረሻ ላይ ሠልፍ ልናካሂድ እንደሆነ ለሚመለከተው አካል የምናሣውቀው እኮ ይሄንን ነገር ጠብቆ ዝግጅት እንዲያደርግ ነው፡፡ ደሞዝ የሚከፈለው የፖሊስ ተቋም ዋናው ሥራው ከቁጥጥር ውጭ የሆኑና ያልተገቡ ነገሮች በግብር ከፋዩ ህዝብ ላይ እንዳፈፀም ነው፡፡ ሠላማዊ ሠልፍ እኮ መብት ነው፡፡ እኛም ለመንግስት አካል የምናሣውቀው በሠልፉ ጊዜ አላግባብ የሆነ አመፅና ሁከት የሚፈጥር ሠው ቢኖር ያንን ለይቶ ሥርዓት የሚያሲዝ እንዲመደብ ነው፡፡ ይሄ የመንግስት ግዴታ እንጂ የሠማያዊ ፓርቲ አይደለም፡፡ አሁን እናንተ ለሚመለከተው አካል አሳውቃችኋል? ማዘጋጃ ቤት ውስጥ የሚገኝ አንድ ቢሮ አለ፤ እንዲያውቀው የሚደረገው ሠልፉ ከመካሄዱ ከ48 ሠዓት በፊት ነው፤ እኛም ጊዜው ሲደርስ ግንቦት 15 አካባቢ እናሣውቃለን፡፡ አሁን ትኩረት ያደረግነው ለህዝቡ በስፋት የማስተዋወቅ የህዝብ ግንኙነት ሥራ ላይ ነው፡፡ ከሠልፉ ምን ትጠብቃላችሁ? ሠልፈኛው ጥቁር እንዲለብስ የፈለጋችሁበት ምክንያት ምንድነው? ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ የሠልፉ አላማ መንግስትን በተደጋጋሚ የጠየቅነው ነገሮች ነበሩ።

በመግለጫው ላይ እንዳመለከትነውም ችግሮቹ ዛሬ የተፈጠሩ አይደሉም፣ በተደጋጋሚ በግልጽ ደብዳቤ ጠይቀናል፣ አቋም ወስደንም በመግለጫ አውጥተናል፡፡ ነገር ግን መንግስት እኛን ከማጥላላት፣ ከማንኳሰስና ጆሮ ዳባ ልበስ ከማለት ውጭ መልስ አልሰጠም፡፡ ስለዚህ አሁንም አላማችን ጥያቄዎቻችን ጆሮ አግኝተው መፍትሔ እንዲሰጥ ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት የስራ አጡ ቁጥር የትየለሌ ነው፣ ኑሮ ውድነቱ አላፈናፍን ብሏል፣ ሙስና ተቋማዊ ሆኗል፣ ጋዜጠኞች እስር ቤት ናቸው፣ የሃይማኖት ጥያቄ የጠየቁ ሰዎች እስር ቤት ናቸው፤ መፈናቀሉን አሁንም አልቆመም፡፡ “ይህን ሁሉ ነገር መልክ አስይዝ” ነው የምንለው፡፡ ምክንያቱም መንግስት ግዴታ አለበት፡፡ ይህን እስኪመልስ አሁንም ግፊታችን ይቀጥላል፡፡ ሠላማዊ ሰልፉ የግፊቱ አንድ አካል ነው፡፡ ህዝቡ ግብር የሚከፍለው መንግስትም የህዝብን ስልጣን የያዘው እነዚህ ችግሮች እንዲፈቱ እኮ ነው፡፡ ይህንን ካላደረገ የማንን ጐፈሬ ሊያበጥር ነው፡፡ ስለዚህ “እባክህ ስማን” ነው እያልን ያለነው። መቼም ሟርት አይደለም፤ ግን ሠላማዊ ሰልፉ እንደከዚህ በቀደሙ ቢከለከል ምን ታደርጋላችሁ? እኔ አሁን ስለመከልከሉ አላስብም፡፡ መብቴ ስለሆነ ሰልፉ ይካሄዳል የሚል እምነት ነው ያለኝ፡፡ የእስከዛሬው የተከለከለው መብታችሁ ስላልሆነ ነው እንዴ? እንደሱ ማለት ሳይሆን ያንን አደረጉት ራሱ መንግስት ይወቀስበታል፡፡ ነገር ግን ገና ለገና እንከለከላለን እያልን እጃችንን አጣጥፈን አንቀመጥም፡፡ እንደባለፈው መታሰር ቢመጣስ ለዚያ ዝግጁ ናችሁ? ያንን እነሱ ናቸው የሚያውቁት፡፡ ይሠሩን፣ ይግደሉን፣ ወይም ከዚህ የተለየ ነገር ያድርጉ፤ ህገ-ወጥ ስለሆነ፣ በቃ ህገ-ወጥ ድርጊት ነው፡፡

ለምሣሌ አንቺ ሠላማዊ ሰው ነሽ፤ ከዚህ ስትወጪ ማጅራት መቼ ቢያገኝሽ ምን ትያለሽ? አንቺ መብት ያለሽ ዜጋ መሆንሽን በሠላም ወጥተሽ መግባት መብትሽ እንደሆነ ነው የምታምኚው፡፡ ነገር ግን እኔ ህጋዊ ስለሆንኩ ሠላማዊ ሰልፍ ማድረግ መብቴ እንደሆነ እኔ ብቻ ሳልሆን እናንተ ጋዜጠኞችም ታውቃላችሁ፤ ስለዚህ እኔ ህጋዊ መሆኔን እንጂ ህገ-ወጦች ስለሚሠሩት ላውቅ አልችልም። እኔ የማውቀው የተፈቀደውን እና ህጋዊውን እንጂ በህገ-ወጥና በውንብድና የሚደረገውን አላውቀውም፡፡ ሠማያዊ ፓርቲን ያፍርሰው፣ ሰብስቦ አመራሩን ይሰረው፣ እንደተለመደው ሌላ አይነት ፋይል ያዘጋጅ፤ ያ የእርሱ ፋንታ ነው፡፡ እንደተለመደው ሌላ አይነት ፋይል ያዘጋጅ ሲሉ ምን ማለትዎት ነው? ጓደኞቻችን ሽብርተኛ ተብለው በየእስር ቤቱ አይደለም እንዴ ያሉት! ጋዜጠኞችና ፖለቲከኞች ማለቴ ነው፡፡ ለምሣሌ እነ አንዷለም አራጌና ጋዜጠኛ ርዕዮት ዓለሙ የቅርብ ጓደኞቼ ናቸው፤ እስር ቤት እንዳሉ ታውቂያለሽ፤ የሽብርተኝነት ፋይል ተዘጋጅቶላቸው አይደለም እንዴ? እና እንዲህ ያለው ነገር ለኢትዮጵያ አዲስ አይደለም። ነገር ግን ይህ እንዲለወጥ ነው ትግላችን፡፡ በሠላማዊ ሠልፉ ላይ ጥቁር ስለመልበስ ጠይቀሽኝ ነበር፡፡ ችግራችንን ሀዘናችንን፣ ያለንበትን አስቸጋሪ ሁኔታ ለማመልከት ነው ጥቁር እንዲለበስ ያስፈለገው፡፡ ከአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ጋር አስታካችሁ ሠልፉን መጥራታችሁ ክብረ በዓሉን አይረብሽም ትላላችሁ? በምንም መንገድ አይገናኝም፡፡

ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ አንቺም እንደምታውቂው ይህ አይነቱ ብሶትን የማሰማት አሰራር በትላልቅ ስብሰባና ኮንፈረንሶች ላይ ይደረጋል፤ በአለም አቀፍ ደረጃ የተለመደ ነው፡፡ ስለዚህ ሰላማዊ ሠልፉ ስብሰባውን ይረብሻል የሚለው ፍፁም የማይገናኝ ነገር ነው፡፡ ፓርቲው ራሱን ለማስተዋወቅ ሠላማዊ ሠልፍ አይጠራም፣ በሠራቸው ሥራዎች በአገር አቀፍም ሆነ በአለም አቀፍ ደረጃ ታውቋል ብለዋል፡፡ እስቲ በዚህ አንድ አመት ውስጥ ምን ምን እንደሠራችሁ ይንገሩኝ…? እንግዲህ አንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር ለመንግስት የአሠራር አቅጣጫ ነድፎ አይሰጥም። ሊያደርግ የሚችለው ፖሊሲውንና ፕሮግራሙን ለህዝብ ማስተዋወቅ፣ ድርጅታዊ ጥንካሬውን መፍጠር፣ አማራጭ ሀይል ሊሆን እንደሚችል ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ፣ ለሲቪክ ማህበረሰቡና ለሌሎች ቡድኖች ማሳወቅ፣ ፓርቲው አመራር መቀበል የሚችል አቅም ያለውና የኢትዮጵያን ችግሮች ሊፈታ የሚችል መሆኑን፣ በአሠራርም በአደረጃጀትም ሆነ በፖሊሲ ደረጃ ከአንድ ተቃዋሚ የሚጠበቀውን በማድረግ ረገድ ፓርቲው ከሚገባው በላይ ከፍተኛ ሥራ ሰርቷል። በተለያዩ አገራዊ አጀንዳዎች ላይ የተለያዩ ውይይቶችን በቢሮው አድርጓል፡፡ ወሳኝ የሆኑ አገራዊ ጥያቄዎችን ይዞ ወደ ህዝብ ወጥቷል። ስለዚህ በእኔ እምነት እንደ አንድ ተቃዋሚና ስልጣን ያልያዘ ፓርቲ የምንችለውን ሁሉ ሠርተናል ብዬ ነው የማምነው፡፡ አዲስ እንደመሆናችሁ ከሌሎች ተፎካካሪ ፓርቲዎች ጋር ያላችሁ ግንኙነት ምን ይመስላል? በጣም ጥሩ ግንኙነት አለን፡፡ በተለያዩ ፓርቲዎች ያሉ ሰዎችንም እናውቃቸዋለን።

አብረናቸው ስንሰራም ነበር፡፡ ለምሣሌ የ33ቱ ፓርቲዎች ውስጥ አለንበት፡፡ ባለፈው ለሁለተኛ ጊዜ የመግባቢያ ሰነድ ከተፈራረምን በኋላ የመጀመሪያውን አብይ ኮሚቴው ስብሰባ ሲያደርግ በሰማያዊ ፓርቲ ጽ/ቤት ውስጥ ነበር፡፡ በአብይ ኮሚቴው በምክትል ፀሐፊነት የሚሠራው የፓርቲያችን ምክትል ሊቀመንበር ነው፡፡ ከአንድነትም ሆነ ከመኢአዶች ጋር መልካም ግንኙነት ነው ያለን፡፡ አሉ ከሚባሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር አብረን እየሠራን ነው፡፡ በመጨረሻ የሚሉት ነገር ካለ …? እንግዲህ ሰልፉ እንደስሙ ሠላማዊ መሆኑን ደጋግመን ገልፀናል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ ሥራ ሃሳብ አመንጭቶ ስትራቴጂ ነድፎ ህዝቡን መምራት ነው፡፡ አንደበቱ ሚዲያ ሲሆን ጉልበቱ ህዝብ ነው፡፡ ውጤት እንዲመጣ ከተፈለገ ከላይ የተጠቀሱት ሶስት ነገሮች መተሳሰር መቻል አለባቸው፡፡ ሚዲያ አንደበት ነው፣ ፓርቲ አዕምሮና መሪ ነው፣ ህዝብ ጉልበት ነው፡፡

ይዘን የተነሳነው የህዝብ ጥያቄ ነው፡፡ እኔ የግል ጥያቄ የለኝም ወይም ሰማያዊ የተለየ ጥያቄ የለውም፡፡ ነገር ግን የዚህ አገር ችግር የህዝብ ችግር ነው፡፡ ጥያቄውን ይዘን መጥተናል፤ ወደ ውጤት የምንመጣው በህዝብ ተሳትፎ ነው፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያዊያን የኢህአዴግ አባላትን ጨምሮ ሁሉም በኑሮ ውድነት ውስጥ ነው፡፡ የተለየ ጥቅም የሚያገኙና ባለስልጣናት ካልሆኑ በስተቀር የኢህአዴግም አባል ሆኖ ብዙ የተቸገረ ሰው እንዳለ እናውቃለን፡፡ ስለዚህ ጉዳዩ ይመለከተናል የሚሉ ሁሉ በሰልፉ ተሣታፊ እንዲሆኑ ጥሪ እናቀርባለን፡፡

የኛ ምኞት ጉዳዩ በሲኖዶስ ደረጃ እንዲታይ ነው

ቅዱስ ኤልያስ ሥልጣን፣ ሃብትና ንብረት አይፈልግም

አልመጣም ብንለውም መጥቷል ብንለውም የምንቀይረው ነገር የለም

ልቦናው ንፁህ ለሆነና እግዚአብሔር ለፈቀደለት ሰው በአካል ይታያል

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን አባል የሆነችበት “ማህበረ ስላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ” የተባለው የጽዋ ማህበር አነጋጋሪ እየሆነ መምጣቱ ይታወቃል፡፡ ማህበሩ ከኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስያሜ አንስቶ መስተካከል ያስፈልጋቸዋል የሚላቸውን ጉዳዮች በይፋ እየገለፀ ነው፡፡ ከሁሉም በላይ የውዝግብ መነሻ የሆነው ግን ቅዱስ ኤልያስ ወደ ምድር ወርዷል ማለቱ ነው። ይህን ትምህርት በስፋት የሚሰጡት ደግሞ አባ ዮሴፍ ብርሃነ ናቸው። አባ ዮሴፍ ብርሃነ በ1984 ዓ.ም ከ4 ኪሎ ዩኒቨርስቲ በፊዚክስ ዲፓርትመንት በዲግሪ ከተመረቁ በኋላ ስለሃይማኖት መማር ስለሚፈልጉ፣ ድግሪያቸውን ስራ ሳይፈልጉበት አስቀምጠውት ደብረ ሊባኖስ ገብተው የቆሎ ትምህርት ተምረው በማጠናቀቅ ለ12 አመታት በጐንደርና በጐጃም ያገለገሉ ሲሆን በ2000 ዓ.ም የካቲት ወር ላይ በቀጥታ ወደ ማህበረ ስላሴ በመምጣት ማስተማር የጀመሩ ናቸው። እንዲሁም ጃማይካ ሁለት ጊዜ ሄደው ገዳም ገድመው የተመለሱ የሃይማኖት አባት ከእነዚህ አነጋጋሪ አጀንዳ ይዘው ብቅ ካሉ የማህበሩ አባላትና ከአባ ዮሴፍ ብርሃነ ጋር የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የማህበሩ አባል በሆኑት በፕሮፌሰር ይስማው አለሙ መኖሪያ ቤት የተለያዩ ጥያቄዎችን ይዞ በመቅረብ ተነጋግሯል፡፡

ኤልያስ ወርዷል እያላችሁ ነው፤ ማነው ኤልያስ?

የትስ ነው ያለው?

ይሄን ጥያቄ ከመመለሴ በፊት አንድ ነጥብ ላንሳ፡፡ ይሄ ማህበር የት የት ተሰብስቧል፤ የት ጉባኤ አድርጓል የሚለውን ካነሳን፣ በእርግጥም “ማህበረ ስላሴ ዘደቂቃ ኤልያስ” ስፍር ቁጥር በሌላቸው ገዳማትና አድባራት ጉባኤ አካሂዷል፡፡ የቅዱስ ኤልያስን መውረድ ለብዙ እልፍ አዕላፍ ምዕመናን ያስተማርንባቸው፣ ማህበሩም በእኩል ተገኝቶ ይህን ጉባኤ ያደረገባቸው በጐጃም፣ በጐንደር፣ በትግራይ ብዙ ገዳማት አሉ፡፡ በአለም ዙሪያም በኢየሩሣሌም፣ በአሜሪካና በብዙ ቦታዎች ላይ ማህበሩ ታላላቅ ጉባኤዎች አድርጓል፡፡ ቅዱስ ኤልያስ መውረዱ ከታወጀበት ጊዜ ወዲህ ማለት ነው፡፡ ይህቺ አራት ኪሎ የምትገኘው እግዚአብሔር የመረጣትና “የቤተልሄም ዋሻ” ተብላ በተሰየመች ቦታ ላይ ነው እስከዛሬ ስንሰባሰብ የነበረው፡፡

ወደ ጥያቄው ስንሄድ ቅዱስ ኤልያስ ማን ነው?

የት ነው ያለው ቢባል ቅዱስ ኤልያስ ማለት ከዛሬ ሶስት ሺህ አመት በፊት እግዚአብሔር ያስነሳው ለእግዚአብሔር አምልኮት ቀናኢ የሆነ ልዩ ክብር የተሰጠው፣ እግዚአብሔር በእሣት ሠረገላ ያሣረገውና በመጨረሻ ዘመን መጥተህ ይሄንን አለም ትፋረዳለህ ብሎ ቃል ኪዳን የሰጠው ነው። እና ጊዜው ደቂቃው የተቆጠረለት ሱባኤ ስለደረሰ በተነገረለት ቀነ ቀጠሮ መሠረት፣ እግዚአብሔር አምላክ በሙሉ ስልጣንና ሃይል ወደዚህ ምድር ልኮታል፡፡ የቅዱስ ኤልያስ መገለጫው ትክክለኛ ቀናኢ የሆነ አምልኮተ እግዚአብሔር ይስፈን የሚለው ነው፡፡ ይሄንን ነው የሚፈልገው፤ በዚህ ይታወቃል፡፡ ሌላ ደግሞ ክፉ ስራ ሲሰራ ዝም ብሎ የሚያይ አይደለም፤ ስልጣንና ሃይል ተሰጥቶታል። ሁለተኛ አስፈሪው ነገር ይሄ ነው፡፡ ተፈጥሮን ማዘዝ ይችላል፡፡ ማንኛውንም ነገር ማከናወን ይችላል፡፡

በእርግጥ ኤልያስን በአካል ማየት ይቻላል? የት ነው ያለው?

አዎ! እግዚአብሔር ፈቅዶላቸው እና ልቦናቸውን ንፁህ ላደረጉ ቅዱስ ኤልያስ ሊያነጋግራቸው ይችላል። እኛ ከልብ የምንወዳቸውና እውነትን እንደሚናገሩ የምናምናቸው በረሃ ላይ ወድቀው ያሉ አባቶቻችን ናቸው ይህ ታላቅ ነቢይ ሰአቱና ደቂቃው ደርሶ ወደዚህ ምድር መምጣቱን የነገሩን፡፡ እና አባቶቻችንን አነጋግሯቸዋል፡፡ እሱ እንግዲህ ረቂቅ እና እሣታዊ ስለሆነ በመላው አለም መንቀሳቀስና ሁሉን ሃይል ማሳየት የሚችል ነው። ልቦናው ንፁህ ለሆነና እግዚአብሔር ለፈቀደለት ሰው በአካል ይታያል፤ ያነጋግራል፡፡ እግዚአብሔር ላልፈቀደለት ግን አይታይም፡፡ ከዚህ ቀደም ብዙ ኤልያስ ነን የሚሉ ግለሰቦች በተለያዩ ሃገራት ተከስተው ነበር፡፡ አሁንም እናንተ የህዝቡን በኑሮ መጨነቅ፣ የፖለቲካ አለመረጋጋቶች፤ እና የመጨረሻው ዘመን ቀርቧል የሚሉትን አመለካከቶች መነሻ አድርጋችሁ ነው ኤልያስ መጥቷል እያላችሁ የምታስተምሩት ይባላል?

እንግዲህ አሁን እኛ ቅዱስ ኤልያስ መጥቷል ስላልን አይመጣም፣ አልመጣም ስላልነውም አይቀርም፡፡ መጥቷል በማለታችን ደግሞ የምናገኘው ትርፍ የለም። አልመጣም ስላልን ደግሞ የምናስቀረው ነገር የለም፡፡ ትልቁ ቁም ነገር ቅዱስ ኤልያስ መጣ ሲባል ምን ማለት ነው የሚለውን መረዳት ነው፡፡ አሁን በቤተክርስቲያናችን ቅዱስ ሚካኤል መጣ እንላለን፡፡ ዳንኤል በአንበሣ ጉድጓድ በተጣለ ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ ከአንበሳ ጉድጓድ አድኖታል፡፡ እነ ሰልስቱ ደቂቅ፤ እሣት ውስጥ ሲጣሉ ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ ከእሣት አድኗቸዋል፡፡ የቅዱስ ኤልያስ መምጣት ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ማንም ቅዱስ እኮ ከገነት ከብሔረ ህያዋን መጥቶ መሄድ ይችላል፡፡ አሁን ዋናው ጉዳይ መጥቷል አልመጣም የሚለው ክርክር አይደለም። የቅዱስ ኤልያስ መምጣት ዘመን፣ ሰአትና ደቂቃ ሲጠበቅለት ነበር፡፡ ያቺ ቀጠሮዋ ስትደርስ በ2000 ዓ.ም መጣ፡፡ መጣ ስንል ምን ማለት ነው፡፡ ለፍርድ ሃይል ለብሶ ስልጣኑ ተሰጥቶት አለምን ለመፋረድ መጣ ማለት ነው፡፡ አሁን በአለም ላይ ያለውን ትልቁን ስልጣን፣ በትረመንግስቱን ቅዱስ ኤልያስ ጨብጦታል፡፡ አለም በፍርድ ላይ ነው ያለችው፡፡ ማስጠንቀቂያ እየተሰጠ ነው፡፡ ትክክለኛውን መንገድ ተከተሉ፣ ሰንበትን አክብሩ፣ እውነተኛውን መስመር ያዙ እያለ ነው፡፡ ከዚህ የወጣውን ግን ይገስፀዋል፡፡ አሁን የኛ ጥረትና አባቶቻችን ያስረዱን ቅዱስ ኤልያስ የሚፈልገው ምንድን ነው የሚለውን ነው። ቅዱስ ኤልያስ ስልጣን አይፈልግም፣ የማንንም ሃብት ንብረት አይፈልግም፣ የሚፈልገው ትክክለኛ አምልኮተ እግዚአብሔር በአለም ላይ እንዲሰፍን ነው፡፡ አለም እሺ በጄ ብሎ ቢቀበል ያን ጊዜ በአክአብ ዘመን እንደነበረው በአለም ላይ ሠላም ይሰፍናል፣ በአንዲት ቅጽበት እግዚአብሔር ታላቅ ተአምራትን ያደርጋል፡፡ ስለዚህ እኛ አለም ሁሉ እንዲሰማው የሰው ልጆች እንዲገነዘቡት የምንፈልገው፣ ቅዱስ ኤልያስ በትልቅ ሃይልና ስልጣን መምጣቱን ነው፣ ማንም ከፍርዱ ሊያመልጥ አይችልም፡፡ አልመጣም ብንለውም መጥቷል ብንለውም እኛ የምንቀይረው ነገር የለም፡፡ እሱ ስልጣኑ ተሰጥቶት መጥቷል፡፡ ስለዚህ እያንዳንዱ መስመር ይያዝ፡፡ ሰንበትን ያክብር፣ እውነተኛ ተዋህዶን፣ ወልደአብ ወልደ አምላክ በተዋህዶ ከበረ፣ አንድ አምላክ አንድ ባህሪ የምትለዋን እውነተኛ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚፈፀምባትን ተከተሉ ጠብቁ እያለ ድምፁን እያሰማ ነው፡፡ አለም ይህን እሺ ብሎ ቢቀበል ከማንኛውም ጭንቀት ሊተርፍ እና ሊድን ይችላል፡፡ ይሄን እምቢ ካለ ግን ከፍርድ ሊያመልጥ አይችልም፡፡ ሌላው መታወቅ ያለበት ቅዱስ ኤልያስ ረዳት አይሻም፤ ለምሣሌ አንድ የፖለቲካ ቡድን ቢቋቋም ገንዘብ አዋጡልኝ ይላል ወይ የሰው ሃይል ስጡኝ ይላል፣ ቅዱስ ኤልያስ ግን ይሄን አይፈልግም፡፡ ተዋህዶ ብቻ ነው የምንከተለው፣ ኦርቶዶክስ የሚለውን አንቀበልም ትላላችሁ፡፡

ምንድን ነው ልዩነቱ?

አሁን ቤተክርስትያኗ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አይደለም እንዴ የምትባለው?

ለምንድን ነው ተዋህዶን ብቻ መነጠል ያስፈለጋችሁ?

ቅባት፣ ፀጋ፣ ሶስት ልደት እየተባለ በቤተክርስቲያናችን ውስጥ ከፍተኛ ችግር አለ። ነገር ግን ትልቁ ቁምነገር ከመጀመሪያው አንስቶ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛዋን ሃይማኖት ካስተማረ በኋላ መናፍቃን ሲነሱ፣ እነ አርዮስ፣ መቅዶንዮስ፣ እነ ንስጥሮስ ሲነሱ፣ አባቶቻችን ጉባኤ ሠርተው እውነተኛዋ ንጽህት የሆነች ተዋህዶን አንድ አካል አንድ ባህሪ ወይም በሊቃውንት አባባል “ወልደ አምላክ ወልደ ማርያም በተዋህዶ ከበረ” የምትለዋን ሃይማኖት መስክረውልናል፤ ደንግገውልናል፡፡ ይህቺን እውነተኛ መስመር ተከትለን እንድንሄድ፣ የሰው ልጅ ድህነት አግኝቶ የዘላለም ህይወት ውስጥ የሚገባው፤ ወደ ዘለለማዊ ህይወት በር የሚሻገረው፣ በዚህች እውነተኛ ጠባብ መስመር ሲጓዝ ነው፡፡ ስለዚህ የተለያዩ ኑፋቄዎች በዙሪያችን ቢኖሩም ከነዚህ ሁሉ ተጠብቀን እውነተኛ መስመር እንድንጓዝ ነው የሚፈለገው፡፡ ነገር ግን አሁን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተብሎ እዚያ ውስጥ ብዙ ኑፋቄ፣ የለየለት ክህደት እንዳለ፣ ውስጥ ለውስጥ ብዙ ክፉ ስራ እንደሚሰራ ሁሉም የሚያውቀውና የሚገነዘበው ነው፡፡ ቀናኢ ነብይ የሆነው ቅዱስ ኤልያስ ከዚህ ሁሉ እንክርዳድ ራሳችንን እንድንጠብቅ፤ እውነተኛ መስመር እንድንከተል ነው ያዘዘን፡፡ ይህ አቋማችሁ ቤተክርስቲያኗን አይከፋፍልም? የእናንተን አካሄድ ኑፋቄ ነው በሚል የሚነቅፉ የሃይማኖቱ መሪዎች አሉ?

ማለት … የቅዱስ ኤልያስን መውረድ ነው ኑፋቄ ነው የሚሉት?

የቅዱስ ኤልያስን መውረድም ሆነ አጠቃላይ የእናንተን አካሄድ ….

አዎ እንግዲህ እሱ አለ፡፡ የተለያየ ነገር እንደሚባል ሰምተናልም አይተናልም፡፡ ነገር ግን ቀደም ብዬ እንዳስረዳሁት ነው፡፡ ይሄ እውነታ ነው፤ እኛ ስለተናገርነው የምንጨምረው ነገር የለም፤ ስላልተናገርን ደግሞ የምንቀንሰው ነገር የለም፡፡ ማንም ሊሸፍነው የማይችለው እውነት ነው፡፡ እግዚአብሔር ፍቃዱ ሆኖ አንድ ጊዜ ቅዱስ ኤልያስ ወርዷል፡፡ አሁን ይህንን ማንም ሊሰውረው አይችልም፤ እኛም ተባብረን እንሰውረው ብንል አንችልም እና ይሄን አስተውሎ እውነቱን መከተል ነው እንጂ ኑፋቄ ነው እያሉ ምክንያት መደርደር ዋጋ የለውም፡፡ ጌታ ሰው በሆነ ጊዜ በዚህ ምድር ላይ ሲመላለስ ምን ነበረ ፀሐፍት ፈሪሳውያን ያሉት፤ “ይሄ ሰውዬ የናዝሬት ሰው ነው፤ ትንቢቱ የተነገረው ከይሁዳ ወገን ነው፣ ከዳዊት ወገን በይሁዳ ይወለዳል ነው የሚለው፤ እሱ ከናዝሬት የመጣ ነው አባቱም ዮሴፍ ነው እናውቀዋለን። ይሄ ሃሰተኛ ነው” ብለው የተቻላቸውን ያህል ተቃውሞ አንስተዋል፡፡ ሆኖም የጌታን ሰው መሆን ሚስጥር ሊሰውሩት አልቻሉም፡፡ እውነትን ወደ ሃሰት ሊቀይሩት አልቻሉም፡፡ አሁንም ኤልያስ መጥቷል፡፡ ኤልያስ የሚመጣው ከኢየሩሣሌም ነው፤ የሚመጣው ከአውሬው ጋር ነው፤ በዚህ ጊዜ ነው ምናምን የሚሉ ብዙ ምክንያቶች ይደረደራሉ፤ ግን ዋጋ የለውም፡፡ እግዚአብሔር በሚስጥር ስራውን አከናውኗል፡፡ ስለዚህ ፀሐፍት ፈሪሣውያን፣ ጌታን ተቃውመው እውነትን መሰወር እንዳልቻሉት፣ አሁንም ብዙ የቤተክርስቲያን ሰዎች ቢናገሩ፣ መጽሐፍት ቢጠቅሱ፣ ይሄንን ሃቅ ሊሰውሩት አይችሉም፡፡ አንዴ እውነቱ ወጥቷል። ትልቁ ቁም ነገር የሰው ልጅ ቆም ብሎ የቅዱስ ኤልያስን መልዕክት አስተውሎ መጓዙ ላይ ነው፤ እንጂ ሃሰተኛ ነው፤ ኑፋቄ ነው፤ ቤተክርስቲያንን ይከፋፍላል ቢባል እውነቱን መሰወር አይቻልም። ልክ ያን ጊዜ ፀሐፍት ፈሪሣውያን ሆነው እንደተገኙት ነው የሚሆነው እንጂ ሌላ ትርጉም አይኖረውም፡፡

ይህ አቋማችሁ ከማህበረ ቤተክርስቲያን ያገለናል የሚል ስጋት የላችሁም?

ቅዱስ ሲኖዶስስ ሊያወግዛችሁ አይችልም?

ይህ እንግዲህ እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ ደርሶ የመወገዝ ነገር እስካሁን የለም፡፡ በቅርቡ ግን መምህር ምህረተአብ አሰፋ ባወጡት ቪሲዲ፤ በተለይ ከየካቲት 28 ጉባኤ በኋላ፣ የጐሉ ተቃውሞዎችን አይተናል፡፡ እኛ ይሄንን መልዕክት መስጠት የጀመርነው ግን ጳጉሜ 1 ቀን 2003 ዓ.ም ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ፤ ለአባቶች፣ ለሲኖዶስ አባላት፣ ለተለያዩ ገዳማዊ አባቶችና መምህራን ትምህርቱን ሰጥተናል፤ ከብዙዎች ጋርም ተማክረናል፤ ከብዙ ደቀመዛሙርትና መምህራን ጋርም ጉዳዩን ተወያይተንበታል። መክረንበታልም። “ማህበረ ስላሴ” በተለያዩ ገዳማትና አድባራት ይህን ጉባኤ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ አሁን እንግዲህ ለሁለት አመት ያህል መሆኑ ነው። እርግጥ ያን ጊዜ ተቃውሞ የለም ማለት አይደለም፤ ሃሰተኛ ነው የሚሉም ነበሩ፡፡ እርግጠኝነቱን ተቀብሎ ዳግም ራሱን ከ“ማህበረስላሴ ዘደቂቅ ኤሊያስ” ጋር አሠልፎ የሚጓዝም አለ፡፡ ግን በሲኖዶስ ደረጃ ነገሩ የታየ አይመስለንም፤ የኛ ምኞት ግን እንዲታይ ነው። እውነቱ እንዲገለፅ ነው፡፡ ለምሣሌ አሁን መምህር ምህረተ አብ የሠጡት ምላሽ፣ የቤተክርስቲያን መልስ አሠጣጥ አይደለም፡፡ የቤተክርስቲያን መልስ አሠጣጥ ከታሪኩ እንደምንረዳው እነ አርዮስም ሲወገዙ ጉባኤ ፊት ይቀርባሉ፤ ሙሉ ሃሣባችሁን ግለፁ ይባላሉ። ለተነሣው ሃሣብ መልስ የሚሠጠው ሙሉ ጥያቄና መልስ ከተካሄደ በኋላ ነው፡፡ ይሄ ስህተት ነው፤ ይሄ እውነት ነው፤ የሚለው ፍርድ የሚሠጠው ከዚያ በኋላ እንጂ አንድ ቃል ቀንጭቦ ማጋጋል አይደለም፤ ይሄ አይነት አካሄድ የአባቶቻችን ይትበሃል እና መስመር አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ፈቃዱ ቢሆን ጳጳሣቱም ሆኑ የቤተክርስቲያን ሃላፊዎቹ አንድ ጉባኤ ሠርተው

“እስቲ ኤልያስ ይመጣል ተብሏል፤ ትንቢቱ እንዲህ ተነግሯል ጊዜው ነው?

መጥቷል ወይንስ አልመጣም?

እስቲ ምንድን ነው ምልክቶቹ?”

ሃሠት እና እውነቱ ሁሉ ለአለም ቢገለፅ የእኛም ምኞት ነው። ብዙዎቹ አሁን ይሄ ሲነገር አዕምሮአቸው የሚሄደው የስልጣን ሽሚያ፣ የሃብት ንጥቂያ ነገሮች ጋ ነው። እውነቱን ለመናገር ይሄን መልዕክት ለኛ እየነገሩን ያሉ አባቶቻችን በባዶ እግራቸው የሚሄዱ፣ እህል የማይቀምሡ፣ ራሣቸውን አሣልፈው ለእግዚአብሔር የሠጡ፣ የዚህን አለም ተድላ የናቁ ናቸው፡፡ ስለዚህ እነሡ መጥተው በጵጵስና በወርቅ ዙፋን ላይ ተቀምጠው የመኖር ሃሣብ የላቸውም፡፡ ሃሣባቸው የእግዚአብሔር አምልኮት በትክክል እንዲፈፀም ብቻ ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ የምትሠባሠቡት ከቤተክርስቲያን ውጪ በአዳራሾች ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቤተክርስቲያን ተቀባይነት እንደሌለው ሊቃውንቱ ያስረዳሉ፡፡ ይህንንም ኑፋቄ ነው ብለው ይነቅፋሉ … እኛ ከቤተክርስቲያን አንድም ቀን ወጥተን አናውቅም። ይሄ እምነታችን ነው፤ እውነተኛም ነው፡፡ ምናልባት ቦታው የካቲት 28 ቀን 2005 ዓ.ም እንዳደረግነው በአዳራሽ ሊሆን ይችላል፡፡ በቤተክርስቲያን ውስጥ ሲባል ሚስጥሩ ሲመረመር ትርጓሜው ቤተክርስቲያን ማለት መንፈስ ቅዱስ የሠፈረበት፣ የደናግል መነኮሣት፣ የሠማዕታት የሃዋሪያት ማህበር ያለበት፣ የእነሡ አስተምህሮ የሚነገርበት፣ እነሡ በመንፈስም በአካልም ተገኝተው የሚባርኩት ጉባኤ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ እኛ ጉባኤያችንን ለእግዚአብሄር አምልኮት ቀናኢ ሆነን እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን ቅዱስ ኤልያስን ይዘን ጉባኤ እስካደረግን ድረስ እኛ ያለነው በእርግጥም በቤተክርስቲያን ውስጥ ነው፤ ቁም ነገሩ ቦታውና ህንፃው አይደለም።

በቤተክርስቲያን ውስጥ ነው ጉባኤያችንን በሙሉ ያደረግነው፤ በአካል ግን በቤተክርስቲያን ውስጥ ለምን አልተደረገም ለሚለው አስቀድሜ መልሻለሁ፡፡ በተለያዩ ገዳማትና አድባራት እንዲሁም በተለያዩ ቦታዎች እየተዟዟርን በምናስተምርበት ጊዜ ቅዳሴው፣ ካህናቱ አሉ፣ ማህሌቱ በተቆመበት ነው ይህ ጉባኤ የሚካሄደው። የቅዱስ ኤልያስ መውረድም የተነገረን እንደዚሁ ነው። እኛ አሁንም ቢሆን በቤተክርስቲያን ውስጥ ነን፡፡ ትሁታን ሆነው ለገዳማት ለቤተክርስቲያናት የተለያዩ እርዳታዎችን የሚያደርጉት ደግሞ በቤተክርስቲያን ውስጥ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እየደገፉ ናቸው፡፡ ስለዚህ ከቤተክርስቲያን ተገልሎና ወጥቶ የራሱን ቡድን አቋቁሞ የሚሄድ ሠው የለም፡፡ ይህ እንደ ፖለቲካዊ ድርጅት የአመፃ አካሄድ አይደለም፡፡ እኛ በእውነተኛ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሆነን ክፉ ነገር ከቤተክርስቲያን ይራቅ ነው የምንለው። እኛ በቤተክርስቲያን ውስጥ መሆናችንን ነው የምናውቀው። ለጊዜው በዚያች ቤት መሠባሠባችንም ሁኔታዎች ስላላተመቻቹ ነው እንጂ እኛ ቤተክርስቲያን መሄድ ጠልተን አይደለም፤ እዚያ የተለያየ ችግር አለ፡፡ እምቢተኝነት አለ፤ ሠአቱም አመቺ አይደለም፤ ማታ ማታ ስለምንሠባሠብ ያለ ሠአት ለምን ትገባላችሁ ትወጣላችሁ ማለት ይመጣል፡፡ ይሄ ሁሉ ችግር ስላለ ነው፡፡ ባጭሩ እኛ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዳለን ነው የምናውቀው፤ አባቶቻችን ከእኛ ጋር ናቸው፡፡ በብዙ ገዳማት አባቶች አሉን፣ ባህታውያን አሉን፣ በጳጳሣት ደረጃም ብዙዎች አሉን፡፡ እኔ ስማቸውን አልጠቅስም ግን ልቦናቸው ከዚህ ጋር የሆነ አብረውን በዚህ እውነት የሚጓዙ በአለም ዙሪያ ብዙ የእግዚአብሔር ወዳጆች አሉ። ከዚህም በላይ በአይን የማይታዩ ቅዱሣን ሁሉ ከእኛ ጋር መሆናቸውን በእርግጠኝነት እናምናለን አምነናልም፡፡

እርስዎ እንደሚሉት ሳይሆን የራሣቸውን ሃይማኖት ፈጥረዋል ነው የምትባሉት?

ከመካከላችሁ “እኔ ኤልያስ ነኝ” የሚል እንዳለም ይነገራል?

ለዚህ እንግዲህ የማቀርበው መልስ መድሃኒታችን ኢየሡስ ክርስቶስ በመጣ ሠአት ከህገ ኦሪት ወደ ህገ ወንጌል አሸጋግሮናል፡፡ ያን ጊዜ መድሃኒታችን ኢየሡስ ክርስቶስ አዲስ ሃይማኖት መስርቷል? ይሄን ነው ለነዚህ ወገኖች እንደ ጥያቄ የምናቀርበው፡፡ ከህገ ኦሪት ወደ ወንጌል ሲሸጋገር አዲስ ሃይማኖት አልመሠረተም። ሃይማኖት አንዲት ነች ለመላዕክት የተሠጠች፣ በህገ ልቦና የነበረች በህገ ኦሪት የተነገረች፣ በህገ ወንጌል የተመሠረተች፣ አለምን አሣልፋ የምትኖር አንዲት ሃይማኖት ነች፡፡ ስለዚህ አሁንም ለዘመናት ትንቢት ሲነገርለት የነበረ ነብይ ነበረ፡፡ ሠአቱ ደቂቃው ደርሶ እሡ ሲመጣ በቤተክርስቲያን ውስጥ ለዘመናት ተሸሽገው ሲሠሩ የነበሩ አጓጉል ነገሮች ነበሩ፡፡ ይሄ በተንኮል ነው የተሠራው፤ መስመሩን እንዲህ አድርጋችሁ አስተካክሉ፣ ቀጥተኛ የቀድሞውን መስመር ተከተሉ ብሎ መስመሩን ቅዱስ ኤልያስ አሣይቶናል፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ኤልያስ የሚፈልገው የቀደመችውን መስመር አጥርተን እንድንሄድ እንጂ አዲስ ሃይማኖትን አይደለም፡፡ ልክ ጌታ፤ ህገ ኦሪት ላይ ተመስርቶ ህገ ወንጌልን ብሩህ አድርጐ እንዳሣየ፣ ኤልያስም ለዘመናት ሲሠሩ የነበሩ ተንኮሎችና አጓጉል መስመሮችን አጥርቶ ትክክለኛውን መስመር እንድናይ አደረገ እንጂ አዲስ ሃይማኖት አይደለም የፈጠረው፡፡ ሃይማኖት አንዲት ናት እሷም ተዋህዶ፡፡ ኤልያስ ወረደ ማለት አዲስ ሃይማኖት አይደለም፡፡

ይልቅስ እነሡ ይወርዳል የሚል መፅሃፍ ነው የያዙት ማድረግ ያለባቸው እንዴትና መቼ የሚለውን በሚገባ መመርመር ነው። በአጭሩ እኛ የመሠረትነው አዲስ ሃይማኖት የለም። በማህበራችን ውስጥም እኔ ኤልያስ ነኝ ያለ አንድም የለም፡፡ ኤልያስ በመላው አለም ቦታና ስፍራ ሣይወስነው በእሣት ሠረገላ ያለ ነው፡፡ ሠንበት ቅዳሜ እንጂ እሁድ አይደለም ትላላችሁ? ይህን ለማለት መነሻችሁ ምንድን ነው? በእርግጥ ሠንበት አንዲት ናት እሷም ቅዳሜ ነች። ይህ እንግዲህ ቅዱስ ኤልያስ ተሠውረው የነበሩ እውነቶችን ሲገልጥ ከተገለጡት አንዱ ነው። ቅዳሜ እና እሁድ ሁለቱም ሠንበት እንዴት ሊባል ቻለ? የሚለውን ከታሪክ መዛግብት በሠፊው ማወቅና መገንዘብ ይቻላል፡፡ ከ4ኛው መቶ አመት ጀምሮ ነው ለ1600 አመታት እሁድ ሠንበት ሲባል የኖረው በተንኮል የገባ ነው፡፡ እግዚአብሔር ስድስት ቀን ፈጥሮ ሠባተኛ ቀን ላይ ያረፈባት ሠንበት ተብላ የተጠራችው ቅዳሜ ነች፡፡ እሁድ እሁድ ነው የራሱ ስም አለው፡፡ እሁድ ብሎ ጀምሮ ቅዳሜ ላይ ያበቃል። በኢትዮጵያም ከታሪክ እንደምንረዳው ሁለት ታላላቅ ጉባኤዎች ተደርገው ሠንበት የትኛው ነው የሚል ጥያቄ ተነስቶ ነበር። ነገስታቱ ማስታረቅ ስላቃታቸው እሁድ ሠንበት ይባል ማለታቸውን ታሪክ ያስረዳናል፡፡ እሁድ የጌታ ትንሣኤ ነው፤ የፅንሠት ቀንም ነው፤ ስለዚህ እሁድን በእሁድነቱ እናከብረዋለን፡፡

አርማችሁ ላይ የዳዊት ኮከብንና የ“ቶ” ምልክትን ነው የምትጠቀሙት ይህ ከአይሁድ እምነት ጋር አይቆራኝም?

እንግዲህ እግዚአብሔር አምላክ ለቅዱሣን ሁሉ ታላላቅ ምልክቶችን ሠጥቷቸዋል፡፡ በእርግጥ እስራኤል ይሄንን የዳዊት ኮከብ የሚባለውንና አሁን በቤተ መንግስታቸው ዙሪያ ያለውን ምልክት ይዘውታል፡፡ በሠንደቅ አላማቸው ላይም ይጠቀማሉ፡፡ ነገር ግን ኮከቡ ራሱን የቻለ ታላቅ ሚስጥር ያለው ነው፤ የመንፈስ ቅዱስ ሃይል ያለው ምልክት ነው፡፡ የስድስቱን ቀን ስነ ፍጥረት ስድስት ጫፎቹ ያስረዳሉ፤ መሃሉ ደግሞ ሠንበትን የሚያመለክት ነው፡፡ “ቶ” ሠባተኛዋ ፊደል ነች፡፡ ሠባት ቁጥር ትልቅ ትርጉም ያላት ነች ፍፁምነትን የምታመለክት ነች፡፡ ሠባተኛው ዙፋን የጌታ እንደሆነ፣ ሠባተኛው ቀን ሠንበት እንደሆነች፣ 7 ቁጥር ብዙ ሚስጥር አላት፡፡ “ቶ” ሠባተኛዋ ቁጥር በመሆኗ ፍፁምነትን የምታመለክት ነች፡፡ ክርስቶስን የምትወክል ነች፡፡ ክርስቶስ ለኛ ሲል በቀራኒዮ መስቀል ላይ ራቁቱን መሠቀሉን የምታመለክት ነች። ትልቁ ከዚህ በላይ ያለው ሚስጥር አባቶቻችን ከቅዱስ ኤልያስ የተረዱት ያን ጊዜ በመላዕክት አለም ውጊያ ተደርጐ ነበር፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ቅዱስ ገብርኤል ከሣጥናኤል ጋር ሲዋጉ ሁለት ጊዜ ተሸንፈዋል፡፡ በሶስተኛው እንዲያሸንፉ ሲልካቸው ይህን ቀስተደመና ቀርፆ፣ ይህን ምልክት የኮከቡን ቅርፅ የ“ቶ” ቅርፅ ያለው መስቀል በየክንፋቸው ቀርፆላቸዋል፡፡ አንዱ የሠጣቸው ትልቅ ሃይል ኮከቡ እና “ቶ” የሚለው ቅርፅ ነው፡፡ ስለዚህ ይህን ተዘንግቶ የነበረውን ቅዱስ ኤልያስ የኛ መሆኑን አውቀን እንድናነሣው አድርጐናል፡፡ ለክርስቲያኖች በሙሉ ዲያብሎስን ድል እንድንነሣበት የተሠጠን ነው እንጂ እንደተባለው ክርስቶስን ከሠቀሉት ጋር የማበርና በእነሡ መስመር የመጓዝ ነገር አይደለም። ነጭ ልብስ ነው መለበስ ያለበት የሚል አዋጅም አውጃችኋል? ይህ ነጭ ልብስና ቀስተ ደመና ያለበት ልብስ ሃይል ነው፡፡ ጥቁር ልብስን በተመለከተ ጥቁር ልብስ አጉል ነገር ነው፡፡ ተንኮል አለበት፡፡ በግብፅ አባቶቻችን ክርስቲያኖች ይኖሩ በነበረ ሠአት በሙስሊሞች ተፅዕኖ ነው ጥቁር ልብስ እንዲለበስ የተደረገው፡፡ ቅዱስ ኤልያስ በዘመናት የተሠራውን ተንኮል ስለሚያውቅ የክርስቲያኖች ልብሳቸው ነጭ መሆን እንዳለበት አውጇል፡፡ ይህም የተሠጣቸውን ተስፋ እና ትንሣኤ የሚያመለክት ነው። ስለዚህ ነው ጥቁር ልብስ ይቅር የሚል ታላቅ አዋጅ ከቅዱስ ኤልያስ የተነገረን፡፡ በተለይ ካህናት ነጭ ወይም ሌላ አይነት ቀለም ያለው ልብስ መልበስ አለባቸው፡፡ ጥቁር ልብስ መልበስ በሠይጣን አገዛዝ ስር ያለን መሆናችንን የሚያመለክት ነው፡፡ ከጥቁር ውጪ ሌላ አይነት መልበስ ይቻላል፡፡ የአንገታችን ማህተብ እና የልብሣችን ዘርፍ የቀስተደመና ቀለም መሆኑም ሃይል ያላብሠናል፡፡

Published in ህብረተሰብ

ባለፈው ሳምንት በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት አካባቢ በርካታ ወጣቶች “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚል ጥቅስ የታተመበት፤ ወይንጠጅ ቀለም ያለው ተመሳሳይ ቲሸርት ለብሰው በጋራ ሲጓዙ ትኩረቴን ሳቡት። እኔ ብቻ ሳልሆን ሌሎች መንገደኞችም በነገሩ መሳባቸው አልቀረም፡፡ አንዳንዶች እንደውም ቀረብ ብለው ሲጠይቁ ሰምቻለሁ፡፡ ለመሆኑ ቲ-ሸርቱ ላይ የሰፈረው ጥቅስ መልዕክት ምንድነው? ሃሳቡን ካመነጩት ስድስት ወጣቶች ጋር ጋዜጠኛ ብርሃኑ ሰሙ ቃለምልልስ አድርጓል፡፡ በቲ-ሸርት ላይ መልእክት ለማስተላለፍ መነሻና ምክንያት የሆናችሁ ምንድነው? የኮተቤ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ የማታ ተማሪዎች ነን፡፡

በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ትምህርት ክፍል ለሦስት ዓመታት የተሰጠንን የአማርኛ ቋንቋ አጠናቀን የዚህ አመት ተመራቂዎች ስለሆንን ደስታችንን በምን እናድምቅው ብለን ስናስብ፣ በአማርኛ ቋንቋ ዙሪያ የሚታይ ችግርን የሚያመለክትና የሚያወያይ መልእክት ማስተላለፍ ስለፈለግን “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚል ጥቅስ በቲ-ሸርት ላይ አሳትመን በመልበስ እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ ምን ያህል ተማሪዎች ናችሁ ለዚህ ዓላማ በጋራ እየተንቀሳቀሳችሁ ያላችሁት? በእኛ ዲፓርትመንት በማታው ክፍለ ጊዜ የምንማር ተማሪዎች ብዛት 116 ስንሆን በሦስት የተለያዩ ክፍሎች ነው የምንማረው፡፡ በምረቃችን ዋዜማ በጥቅስ መልእክት የማስተላለፉ ሀሳብ የመነጨው በአንደኛው ክፍል በምንገኝ ስድስት ጓደኛሞች ቢሆንም አሁን ሁሉም የማታው ክፍለ ጊዜ ተመራቂ ተማሪዎች ደግፈውት በጋራ እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ አማርኛ ቋንቋ ላይ ተጋርጧል የምትሉት ችግር ምንድነው? ቋንቋው ላይ ችግር ተከስቷል ብለን ግንዛቤ ለማስጨበጥ በጋራ እየተንቀሳቀስን ካለነው ተመራቂ ተማሪዎች መሀል አንዳንዶቻችን በግልም፣ በመንግሥትም ትምህርት ቤቶች ስለምናስተምር በተግባር ብዙ ችግር በየእለቱ እናያለን፡፡

ተማሪዎች በትምህርት ቤት ግቢ ወስጥ አማርኛ ቋንቋ እንዳይናገሩ የሚከለክሉ ትምህርት ቤቶች አሉ፡፡ በአማርኛ ቋንቋ የሚናገር ተማሪ ሀፍረት እንዲሰማው የሚያደርግ ተግባር ሲፈፀምባቸው ይታያል፡፡ አማርኛ ቋንቋ ከትምህርት ቤቱ ግቢ በ200 ሜትር ርቀት ብቻ ነው መናገር የሚቻለው የሚል ሕግ ያወጡ ትምህርት ቤቶችም አሉ፡፡ ወላጆች የትኛው ትምህርት ቤት ነው እንግሊዝኛ ጥሩ የሚያስተምረው እያሉ ነው ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤት የሚያስገቡት፡፡ ይህ ልማድ በጊዜ ካልተቀጨ በጥቂት አመታት ውስጥ ወጣቶች ለማንነት ቀውስ ችግር መጋለጣቸው አይቀርም፡፡ ይህ አደጋ መነጋገሪያ እንዲሆን በመሻት ነው እኛም ጥቅሱን አሳትመን በመልበስ በመንቀሳቀስ ላይ ያለነው፡፡ ቋንቋው በንግግር ብቻ ሳይሆን ለፅሁፍም ከማገልገሉ ጋር በተያያዘ ተከስቷል የምትሉት ችግር አለ? አማርኛ፤ እንግሊዝኛ ቋንቋ እያሳደረበት ባለው ጫና ምክንያት ለችግር መጋለጡን ለሕብረተሰቡ እያመለከቱ ያሉ ሌሎች አካላትም አሉ፡፡ በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙሃን የቋንቋ አጠቃቀም ዙሪያ በጌታቸው በልዩ የተሰራ ጥናት አለ፡፡

ከሌሎች የአገራችን ቋንቋዎች በተሻለ ሁኔታም በአማርኛ ቋንቋ ዙሪያ ብዙ ጥናት ተሰርቷል፡፡ እንዲህም ሆኖ የአውሮፓውያን አስተሳሰብ በተለያየ መልኩ ጫና እያሳደረብን እንዳለው ሁሉ፣ ቋንቋችን ዋነኛው ሰለባ እየሆነ መምጣቱ በትምህርት ቤቶች ብቻ ሳይሆን በተለያዩ እለታዊ እንቅስቃሴዎቻችን ውስጥ ይታያል፡፡ “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚለው መልእክታችን አማርኛ ቋንቋን ማዕከል ያደረገ ቢሆንም ሌሎች የአገራችን ቋንቋዎችንም ይመለከታል፡፡ ቋንቋ መግባቢያ ብቻ ሳይሆን ባህል፣ እምነት፣ ወግ፣ ልማድ፣ መከባበር፣ መተሳሰብ፣ ሀዘን ደስታ… መግለጫ ነው፡፡ የራስን ቋንቋ እንደሚገባው አለማወቅ ለማንነት ቀውስ ችግር ይዳርጋል የምንለው ለዚህ ነው፡፡ አማርኛ የፌደራሉ መንግሥት የሥራ ቋንቋ ነው፡፡ በአገራችን ልጆች አፋቸውን በፈቱበት ቋንቋ እንዲማሩ ተወስኗል፡፡ በአዲስ አበባ የሚወለድ ልጅ አፉን የሚፈታው በአማርኛ ቢሆንም በትምህርት ቤቶች ግን በእንግሊዝኛ ቋንቋ የላቀ ችሎታ እንዲኖረው እየተሰራ ወይም የወላጆች ፍላጐት እንደዚያ እንዲሆን የመፈለግ አዝማሚያ በስፋት ይታያል፡፡ ይህ ጅማሬ በዚሁ መልኩ እያደገ ከሄደ በማንነታችን ላይ ጉዳት ማስከተሉ አይቀርም፡፡

በየእለቱ ቅላፄያቸው ወደ እንግሊዝኛ ቋንቋ የተለወጡ የአማርኛ ቃላትን እንሰማለን፡፡ በሙዚቃችን ውስጥ እንዲህ አይነቱ ነገር እየበዛ መጥቷል፡፡ የተማሩ የሚባሉ ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ ፊደል ያልቆጠሩ እናቶቻችንም በንግግሮቻቸው መሀል ብዙ የእንግሊዝኛ ቃላት ሲጠቀሙ እየሰማን ነው፡፡ ቋንቋ የሚፈጠረውና የሚያድገው አንዱ ከሌላው እየወሰደና እየሰጠ ስለሆነ እንዲህ መሆኑ ምን ይገርማል? ችግሩ መቀባበሉ ላይ ሳይሆን አወሳሰዱ ላይ ነው፡፡ ሁሉም ቋንቋ ሀሳብን ለመግለፅ በራሱ ምሉዕ ነው ተብሎ ይታመናል፡፡ አማርኛ ቋንቋ በአባባል፣ በተረት፣ በእንቆቅልሽ፣ በሥነቃል የዳበረና ሀሳብን ለመግለፅ ምንም ችግር የሌለበት ሆኖ ሳለ፣ በንግግር መሐል እንግሊዝኛ ቃላትን መጠቀም አዋቂና የተማረ ያሰኛል ስለሚባል፤ ፋይዳቸው ምንም የሆነ የእንግሊዝኛ ቃላት በአማርኛ መሀል መጨመር ተለምዷል፡፡ ለምሳሌ ተማሪዎቻችንን ለፈተና እየተዘጋጃችሁ ነው? ብለን ስንጠይቃቸው “ዌል ዝግጁ ነን” የሚል መልስ ይሰጡናል፡፡ በዚህ መልስ ውስጥ “ዌል” የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል መጨመሩ ያስገኘው ምንም ጥቅም የለም፡፡ በአማርኛ ቋንቋ ውስጥ ከሌሎች ቋንቋዎች ወስደን የምንገለገልባቸው ብዙ ቃላት አሉ፡፡ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ የሚሉትን ቃላት እንደምሳሌ መጥቀስ እንችላለን፡፡

የቴክኖሎጂ ስያሜዎች ወደ አገራችን ሲገቡ በአገራችን አባባል የሚተረጉም አካል አለመኖሩ ለችግሩ የራሱ የሆነ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ለምሳሌ ጀርመኖች የቴክኖሎጂ ቃላትን በራሳቸው አባባል ተርጉመው የቋንቋቸው አካል ያደርጋሉ፡፡ በእኛ አገር ሲሆን የሚታየው ግን ከዚህ በተቃራኒ ነው፡፡ ከቴክኖሎጂ ማደግ ጋር የሚፈጠሩ ስያሜዎች በየእለቱ ወደ ቋንቋዎቻችን ይገባሉ። ከዚህም ባሻገር ከበድ ያሉ ፅንሰ ሀሳቦችን ተጨማሪ ማብራሪያ ለማያስፈልጋቸው አባባልና አገላለፆች ሁሉ የእንግሊዝኛ ቃላትን መጠቀም እየበዛ መጥቷል፡፡ የተቀላቀለ ቋንቋ የሚናገር ሰው በበዛ ቁጥር ቅይጥ ማንነት ያላቸው ሰዎች ይበረክታሉ፡፡ የአማርኛ ቋንቋም የመጥፋት አደጋ እንደተጋረጠበት ይነገራል፡፡ በእኛም አገር “እንግአማ” ላይ ይወድቃል፡፡ ሂንዱ የሚባለው የሕንዶች ቋንቋ በእንግሊዝኛ ተፅእኖ ስር ወድቆ የመጥፋት አደጋ እየተፈጠረ ስለሆነ “ሳይቃጠል በቅጠል” እንደሚባለው መፍጠን ይኖርብናል፡፡ “እንግአማ” ምንድነው? እንግሊዝኛና አማርኛ ከሚሉት ሁለት ቃላት ተውጣጥቶ የተገኘ ቃል ሲሆን በሁለቱ ቃላት የተመሰረተ አዲስ ቋንቋ ለማለት ነው፡፡ አንድ ሰው ሁለት ማንነት ሊኖረው አይችልም፡፡ “እንግአማ” ሁለት ማንነት ይፈጥራል፡፡ አማርኛ ቋንቋ በዘይቤ የወሎ፣ የጐንደር፣ የጐጃም፣ የሰሜን እና የሸዋ በሚል በአምስት የተለያዩ ክፍሎች ይመደባል፡፡ የገጠር አማርኛ ተናጋሪዎች ሁሉ የእንግሊዝኛ ቃላትን እየደረቱ ሲጠቀሙ መስማት ተለምዷል፡፡ ቋንቋችን ጉራማይሌ ከሆነ ማንነታችንም ጉራማይሌ ይሆናል። አንድ የሬዲዮ ጋዜጠኛ “Part of the body” የሚለውን የእንግሊዝኛ ሐረግ ተናግሮ አብሮት ለሚወያየው የሥራ ባልደረባው “በአማርኛ ምንድነው የሚባለው?” ብሎ ትርጉም ሲጠይቀው ሰምተናል፡፡

ችግሩ እስከዚህ ድረስ ሰፍቶ የሚታይ ነው፡፡ እኛ እንግሊዝኛ ቋንቋን እያጥላላን አይደለም። እንግሊዝኛን ማወቅ የለብንም አላልንም። እንግሊዝኛን ብቻ ሳይሆን ሌሎች የአገርና የዓለም ቋንቋዎችንም ማወቅ ብንችል አንጐዳም፡፡ ማንነታችን ላይ ቆመን ሌላውን ለማወቅ ካልጣርን ግን ጉራማይሌ ማንነት ነው የሚኖረን፡፡ በአገር ውስጥ በሌሎች ቋንቋዎች ጫና ምክንያት ጉዳት ሲደርስበት የሚከላከልለት የሌለ የሚመስለው አማርኛ ቋንቋ፤ አሜሪካንን በመሳሰሉ ኢትዮጵያዊያን በብዛት በሚኖሩባቸው አገራት እንግሊዝኛን አሸንፎ ለመነጋገሪያነት መዋሉን እንሰማለን፡፡ ቻይናም በአገሯ በዩኒቨርስቲ ደረጃ ዜጐቿ እንዲማሩ እያደረገች ነው፡፡ ሌሎች ይህን ያህል ዋጋ ከሰጡት እኛ ከነሱ በላይ ልናከብረውና ልንጠነቀቅለት ይገባል፡፡ የአማርኛ ቋንቋ ትምህርት በአገር ውስጥ በተለያዩ የትምህርት ተቋማት ይሰጣል፡፡ የተለያዩ መፃህፍትም ይታተማሉ፡፡ ቋንቋውን ለመጠበቅና ለማዳን በተለይ ሕብረተሰቡን ማዕከል ያደረገ ሰፊ ሥራ መሰራት ይኖርበታል፡፡ ለዓላማችሁ ድጋፉን የሰጠ ማን አለ? ተቃውሞስ አልገጠማችሁም? ያለውን አደጋ መከላከል የሚያስችል ግንዛቤ ለማስጨበጥ ስንነሳ መምህር ደብሬ “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚለውን ጥቅስ በመስጠት ተባብራናለች፡፡

መምህር የሻው ተሰማን መሰል መምህራንም ጥሩ ነው በማለት አበረታተውናል፡፡ ጥቅስ የታተመበትን ቲ-ሸርት ለብሰን በየአደባባዩ ስንንቀሳቀስ የሚያዩን ሰዎች ዓላማችንን እየጠየቁን ስንነግራቸው እንድንበረታና ሀሳቡን ለሚመለከታቸው አካላት እንድናደርስ በርቱ ይሉናል፡፡ ተቃውሞ ግን እስካሁን አልገጠመንም፡፡ ተመርቃችሁ ከወጣችሁ በኋላስ ለዚህ ዓላማችሁ ለመንቀሳቀስ ምን እድልና ተስፋ አላችሁ? አብዛኞቻችን አስተማሪ ስለምንሆን በተማሪዎቻችንና በትምህርት ቤታችን አካባቢ የምንሰራው ነገር ይኖራል፡፡ ስብስባችንም ሳይበታተን ለዚሁ ዓላማ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር የእግር ጉዞን መሰል የቅስቀሳ መድረኮች የማሰናዳትም እቅድ አለን። የምረቃችንን ዋዜማ በጭፈራና ሆይ ሆይታ ሳይሆን እንዲህ ባለ ቁምነገር ላይ ማሳለፋችንም እያስደሰተን ነው፡፡

Published in ህብረተሰብ

“ዓለምን የቸገራት ምንድን ነው? ምግብ? ልብስ? ቤት? አዎን፤ በሙሉም ባይሆን በከፊል የነዚህ ነገሮች ችግር አለባት፡፡ …ነገር ግን እስካሁን ድረስ መድኃኒት ያልተገኘለት ችግር የመልካም ሰዎች ማነስ ነው” ይላል አቤ መስከረም 10 ቀን 1957 ዓ.ም ለ4ኛ ጊዜ ባሳተመውና “ምልከዓም ሰይፈ ነበልባል” የሚል ርዕስ በሰጠው መጽሐፉ፡፡ ምልክዓም ሰይፈ ነበልባል ከ”አልወለድም” እና “አንድ ለእናቱ” ቀጥሎ ብዙ አንባቢ ያገኘ መጽሐፍ መሆኑን አዲስ ዘመን ጋዜጣ በወቅቱ መዘገቡን አንብቤያለሁ፡፡ ምልክዓም ሰይፈ ነበልባል የመጽሐፉ ርዕስ ብቻ ሳይሆን ዋና ወኪል ባለታሪክም (ገፀ ባህርይ የሚባለው) ነው፡፡ አቤ፤ ሰዎች መብታቸውን ማስከበር ያለባቸው ከተወለዱና ካደጉ በኋላ ብቻ ሳይሆን ገና በእናታቸው ማህፀን ሳሉ…“እውነት በሌለበት ዓለም ለመኖር አልወለድም” ብለው እንዲሟገቱ የጻፈና በዚህም፤ መጽሐፉ ለእሳት፣ እሱ ደግሞ ለቁም እስር፣ ለግዞትና ለእንግልት የተዳረገ ጽኑዕ ደራሲ ነበር፡፡ “አልወለድም” የሚል ተዓምረኛ ፅንስ ፈጥሮ እንዳሳየን ሁሉ “ምልክዓም” የተባለ ሰው “ቤትኤሌፋኦስ” ብሎ በጠራት ሀገር ፈጥሮና በፕሮቴስታንት ሚሲዮን ስርዓት አሳድጐ ለጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ ያበቃዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራትን አገር ህዝብ ሁሉ ስለሚወድና እንደቤተሰቡ ስለሚያምን በሚወዳቸው ሰዎች አማካይነት የተመረዘ ምግብ ይበላና ይሞታል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሊሞት ሲያጣጥር በኑዛዜ መልክ የተናገረውንና በህይወት እያለ “ለፓርላማ እያቀረበ ያስፀደቃቸው ናቸው” ብሎ ነው አቤ ዝርዝር ዕቅዶችንና የተደረጉ ክርክሮችን በዝርዝር ያሳየን፡፡ መጽሐፉ የሚጀምረው ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የ”ውጭ ነፍስ፣ ግቢ ነፍስ” ጣር ላይ ነው፡፡ ከዚያም በህይወት ታሪክ መልክ መልእክቱን ያስተላልፍልናል። ምልክዓም ያገሩን ህዝብ በእጅጉ የሚወድና “ፈጣን ለውጥ” ማምጣት የሚፈልግ፣ በርካታ የለውጥ እርምጃዎችን ወስዶም በአገሩ ህዝብ ዘንድ ተወድዶ የሚከበር ጠቅላይ ሚኒስትር ነበር፡፡ “እኛ ከታላቅ ግብ የምንደርሰው በነፃነትና በኅብረት በምንሠራው ጠንካራ ሥራ ብቻ እንጂ የአንዳንድ መንግሥታት ጥሩንባዎች ሆነን በምናገኘው ምጽዋት አይደለም፡፡ እኛ ነፃ ሕዝብ ነን፡፡

የሚወዱንን የማንወድበት፣ የሚጫኑንን የማንቃወምበት ምክንያት የለንም” ይላል ምልክዓም የውጭ ፖሊሲውን አስመልክቶ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም “ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ዕርዳታና ብድር እንድንፈቅድላችሁ ዝለሉ ሊል ይችላል፡፡ ቶሎ ብለው “ስንት ጊዜ እንዝለል?” የሚል ጥያቄ የሚያቀርቡ መንግሥታት ይኖራሉ፡፡ አኛ ግን ቢያንስ “ለምን? ብለን እንጠይቃለን፡፡” ሲሉ አድምጠናቸዋል፡፡ ምልክዓም በሀገረ ቤትኤልፋኦስ ውስጥ “ፈጣን ለውጥ” ለማምጣት ሌት ከቀን ይሰራ ነበር፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም “ፈጣን ለውጥ” የሚሉትን ቃላት እንደ ዳዊት ከመደጋገም አልፈው በተግባር ለመተርጐም ደፋ ቀና ሲሉ ሞት ቀደማቸው፡፡ “ግማሾች ወገኖቼ በቁንጣን፤ ግማሾቹ በረሃብ ሲሞቱ ለማየት አልሻም፡፡ በሚገባ ሁኔታ ማደላደል፤ ቁንጣንንም ረሃብንም ማጥፋት ስለሚቻል ሁሉንም በሚገባ ለማደላደል ዝግጁ ነኝ” ይላል የአቤው ጠቅላይ ሚኒስትር ምልክዓም፡፡ በሶሻሊዝም ደቀመዝሙርነታቸው የሚታወቁት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም፤ በአገሪቱ ውስጥ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል እንዲኖር ተግተው እንደሚሰሩ፤ በተለይ አዲስ አበባን አሁን ካለችበት ሶስት ደረጃ ወደ ሁለት ለማጠጋጋት እንደሚጥሩ ሲገልጹ ነበር፡፡ ንግግራቸውን በተግባር ለመግለጥም የጋራ መኖሪያ ህንፃዎች በብዛት እንዲሰሩ ፓርቲያቸው ዕቅድ ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ነበር፤ ነውም፡፡

የምልክዓምን ዋና ዋና ተግባራት በተመለከተ ደራሲው (አቤ ጉበኛ) እንዲህ ይገልፀዋል፡፡ “አምስት ዋና ዋና ግድቦች” አሰርቶ የኤሌክትሪክ ቢያዎች በብዛት እንዲቋቋሙና የመስኖ ልማት በጣም እንዲስፋፋ አደረገ፡፡ አርባ ታላላቅ ፋብሪካዎች፣ ስምንት መቶ ቀላል ኢንዱስትሪዎች፣ 550 ታላላቅ የማህበር እርሻዎች እንዲቋቋሙ አደረገ፤ ሁለት የብረት ማቅለጫ፣ አንድ የመዳብ ማቅለጫ ጣቢያዎችንም አቋቋመ፡፡ ከሶስት ቦታዎች ላይ የነዳጅ ዘይት ፍለጋ ሥራ እንዲጀመር አድርጐ ፍለጋው ታላቅ ተስፋ ባለው ሁኔታ ይጣደፍ ነበር” ኢህአዴግም ከዚህ በላይ የተጠቀሱትንና “ምልክዓም አከናወናቸው” የተባሉትን ተግባራት የመሰሉ የኃይል ማመንጫ፣ ፋብሪካ፣ የመስኖ ግድብና የነዳጅ ዘይት ፍለጋ ተግባራትን ትኩረት ሰጥቶ እያከናወነ ይገኛል፡፡ “ትምህርት ቤቶች በሁለት ዕጥፍ እንዲጨምሩ አደረገ፡፡ የሃገሩ አውራጃዎች በባቡር እንዲገናኙ ከማድረጉ በላይ በአንዳንድ ቀበሌዎችም የባቡር ሃዲድ መዘርጋት እንዲጀመር አስደርጓል” (ገፅ 27) በዘመነ ኢህአዴግም ትምህርት ቤቶች በእያንዳንዱ ቀበሌ ገበሬ ማህበር ከመሰራታቸው በተጨማሪ የዩኒቨርሲቲዎች ቁጥር ከሁለት ወደ ሰላሳ አንድ እንዲያሻቅብ አድርጓል፡፡ የባቡር መስመሩም እንደ አቤ ጉበኛው ምልክዓም ተጠናቅቆ ስራ ላይ ባናየውም ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት፤ እንዲያውም በአምስት ዓመቱ የለውጥና የተሃድሶ ዕቅድ ዘመን ውስጥ አምስት ሺህ ኪሎሜትር ሃዲድ ለመዘርጋት አቅዶ እየሰራ ነው፡፡ ግን ከሥራ ዘመኑ ላይ አቤ እና ኢህአዴግ የሚለዩበት መስመር አለ፡፡ የአቤው ምልክዓም ያንን ሁሉ ተግባር ያከናወነው በስልጣን ላይ በቆየባቸው 13 ዓመታት ሲሆን ኢህአዴግ ሊገነባ ያሰበው በአምስት ዓመታት ብቻ ነው፡፡

እርግጥ ኢህአዴግ 11 የሥልጣን ዘመናቱን የፈጀው በስብሰባና አገርን በማረጋጋት ላይ ነው (ከ1983-1994)፤ ከ1995 ዓ.ም በኋላ በተለይም ከ1997 ዓ.ምህረቱ የምርጫ ውጤት ጋር ተያይዞ ከእንቅልፉ ሊባንንና የሚታይ የልማት ውጤት ለማስመዝገብ ችሏል፡፡ “ህዝብ ወዶ ሲጠላኝ ከማየት አለመኖሬን እመርጣለሁ፡፡ …ተወዶ እንደመጠላት ተከብሮ በገዛ ተግባር እንደመናቅ ያለ የሞት ሞት ወዴት አለ” የሚለው ምልክዓም ፤ በራስ ጥረት ማደግ እንደሚቻል ጠንካራ እምነት ነበረው፡፡ መራሔ ኢህአዴጉ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም፤ ዘላቂ ልማት የሚመጣው በሃገሬው ህዝብ ጠንካራ ጥረትና የተባበረ ትግል እንጂ በውጭ መንግሥታት ዕርዳታና ብድር አለመሆኑን ይናገሩ ነበር፡፡ ለማስረጃም ታላቁን የህዳሴ ግድብ በእኛው መዋጮና አቅም ለመገንባት መሠረቱን ጥለዋል፡፡ “አንድ አገር የተፈጥሮ ሃብቶቹን ለተወላጆቹ በበቂ ሊሰጥ ካልቻለ አገርነቱ ብቻ ሊያኮራ አይችልም። ለተራበና የዕለት ፍላጐቶቹን ካላገኘ ሰው ሀገርና ነፃነት ከሚለው ቃል ይልቅ ምግብና ልብስ የሚለው ቃል ይሰማዋል” ይላል ምልክዓም የሀገርን ትርጉምና የህዝብን ሀገራዊ ቁርኝት ሲገልጽ፡፡ ምልክዓም አስተዳደርን አስመልክቶም “ማንም ህዝብ ሥነ ሥርዓት ያለው አስተዳደር፣ ትክክለኛ ፍርድና ፀጥታ ያለው ኑሮ ከነፃነት ጋር ካላገኘ ምንም ነገር ሊሠራ አይችልም” የሚል አቋም ነበረው፡፡ ኢህአዴግም ምንም እንኳን ሃሳቡን በገቢር መግለጽ አቅቶት እየተንገዳገደ ቢገኝም “መልካም አስተዳደር የልማት መሠረት ነው” ብሎ እንደሚያምን ደጋግሞ ሲናገር ይደመጣል፡፡

እንዲያውም ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ጉቦኞችንና ለመልካም አስተዳደር ጠንቅ የሆኑትን ሰላቢዎች በሁለት በመክፈል “የመንግስትና የግል ሌቦች” ብለው መናገራቸው አይዘነጋም፡፡ ምልክዓም ዳቦንና ኑክሊዬርን በማነፃፀርም እንዲህ ብሎ ነበር “ያገራችን ህዝብ ሁሉ በቀላሉ ሊሠራቸው የሚችላቸውን ሥራዎች በተፋጠነና ጠቃሚ በሆነ መንገድ በመሥራት እንድንበለጽግ ነው፡፡ ከአቶሚክ ቦንብ ይልቅ ዳቦ ብዙ ፈላጊ አለው። ግዴላችሁም ሞኝ አንሁን፡፡ በዓለም ውስጥ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ሕዝቦች በረሃብ የሚሰቃዩት ምግብ ስላነሰ እንጂ የኒክሊዬር ቦምብ ስለጠፋ አይደለም” ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም የኢትዮጵያ ሕዝብ ቀንደኛ ጠላት ድህነት መሆኑን፣ ይህንን መሠረታዊ ጠላት ለማሸነፍም ከትጥቅ ትግሉ በላይ መራራ ትግል እንደሚጠይቅ ደጋግመው ይናገሩ ነበር፡፡ “የሀገራችንን ሕዝብ ሠርቶ እንዳይጠቀም እያሰናከልን ‘አገራችን ለውጭ አገር ዜጐች ክፍት ናት፡፡ እንግዳ ተቀባዮች ነን፡፡ ብዙ የውጭ አገር ዜጐች በሀገራችን ውስጥ በደስታ ይኖራሉ’ በሚሉ የራስ ማታለያ ቃሎች ራሳችንን እየሸንገልን በሀገራችን ያሉትን ጠቃሚ ጠቃሚ የሥራ ቦታዎች ለውጭ ዜጐች ብንሰጥ ሕዝቡ አውቆ ሊቃወመን ባይችል እንኳ እግዚአብሔር ይፈርድብናል” ይል ነበር ምልክዓም፡፡ ይህን ድርጊትም ኢህአዴግ እየፈፀመው ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም በየክልሉ ለውጭ ዜጐች ዓይናቸው ያየውንና ልባቸው የከጀለውን ያህል መሬት እየሰጠ፤ ዜጐቹን ግን “ደን ጨፍጭፈዋል” በሚል የዋህ ሰበብ ከደቡብ፣ ከኦሮሚያ እና ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በጠራራ ፀሐይ ሲያፈናቅልና ሲያባርር ተስተውሏል፡፡

አረብና ፓኪስታን መጥቶ በግሬደር ድራሽ አባቱን የሚያጠፋው ዛፍ ግን የኢትዮጵያ ሃብት አይደለም፡፡ ወይም ጥፋት የሚሆነው በኢትዮጵያውያን መጥረቢያ ሲቆረጥ ብቻ ነው፡፡ “አገራችንን ማልማት የሁላችንም ተግባር ስለሆነ ለዚህ ተግባር ከየግል ጥቅማችን በከፊል ለጥቂት ጊዜ መስዋዕት ማድረግ ግዳጃችን ነው፡፡ ብዙ ደሞዝ ያለን ከደሞዛችን እየቀነስን ለልማት ባጀታችን ማሙያ የገቢ ምንጭ መፍጠር አለብን፡፡ …40 ሚሊዮን የሆንን ያገራችን ሰዎች በዓመት አንዳንድ ብር ብናወጣ 40 ሚሊዮን ብር እናገኛለን፡፡ በዚህ በአንድ ዓመት በሚገኘው ብቻ ብዙ ክሊኒኮች፣ ብዙ ትምህርት ቤቶችና አንዳንድ መንገዶች መሥራት እንችላለን” (ገፅ 49፣ 50፣ 100-101) ኢህአዴግም ለሚያከናውነው የልማት ተግባር የአርሶ አደሩ ጉልበትና የከተማ ነዋሪው መዋጮ ከፍተኛ ዋጋ አላቸው ብሎ ያምናል፤ አምኖም ተግባራዊ እያደረገው ነው፡፡ የአቤ ጉበኛው ምልክዓም ስንፍናንም ይኮንን ነበር “የማይሠሩት የሚሠሩትን የሚንቁበትና የሚያጠቁበት ጊዜ አልፏል፡፡ ሠራተኞቻችን ትሁት የሆነ ንቃት መንቃት አለባቸው፡፡ ጨዋ የሆነ ደስታ መደሰትም ይገባቸዋል፡፡” (ገፅ 77) የሥራን ክቡርነት፣ የተመጻዳቂነትን መርዘኛነት ደርግ ገላልጦ ቢያሳይም ኢህአዴግ በተግባር አውሎታል፡፡ ዛሬ በየሰፈሩ ተደራጅተው ደረቅ ቆሻሻ የሚያነሱ፣ በጥርብ ድንጋይ ንጣፍ ህይወታቸውን የሚመሩ በርካታ ወጣቶችን ማየት የተለመደ ሆኗል።

ህዝቡ ቀልጣፋ አገልግሎት የሚያገኝበትን መንገድም ምልክዓም ተልሞ ነበር፡፡ “አንድ ባለጉዳይ ለማንኛውም የመንግሥት መ/ቤት ጉዳዩን ሲያመለክት በጠየቀበት ቀን መልስ ማግኘት አለበት” የሚሉና ሌሎች መሠረታዊ የአሠራር መመሪያዎችን ከማውጣቱም በላይ ለተግባራዊነቱ የቅጣት ህጐችንም አውጥቷል፡፡ ኢህአዴግም ምንም እንኳ በጽናት ባይቀጥልበትና የራሱን ሌቦች መቆጣጠር ባይችልም መሠረታዊ የአሠራር ለውጥ (ቢ.ፒ.አር) አካሂዶ በአንዳንድ መ/ቤቶች፣ ለምሳሌ ውልና ማስረጃና ኢሚግሬሽንና የዜግነት ጉዳይ ተቋማት የሚያስመሰግን ውጤት አሳይተው ነበር፡፡ ክትትል ባለመኖሩ ግን ወደነበሩበት ጐታታ አሠራር ተመልሰዋል፡፡ “…የግል ጠላቱን በመንግሥቱ ክብር ህግ ተጠግቶ የሚያጠቃ አገረ ገዥ፣ ዳኛ፣ ፖሊስ ወዮለት! ለሕዝብ አገልግሎት፤ ወንጀልን ለማስወገድና የሕዝብን መብትና ፀጥታ ለማስከበር ተመርጦ ራሱ የወንጀል መሪ የሆነ ባለሥልጣን ወዮለት” ሲል ምልክዓም ወስላታ ባለስልጣናቱን ያስጠነቅቅ ነበር፡፡ ኢህአዴግም ጠንከር ያለ እርምጃ መውሰድ አልቻለም እንጂ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካይነት “የእኛ ሌቦች” እያለ ባለሥልጣናቱን ሲወርፍ ይደመጥ ነበር፡፡ “ኪራይ ሰብሳቢ” የሚል የበረሃ ስምም አውጥቶላቸዋል፡፡ “የሰይጣን ሕግ ከእግዚአብሔር ሕግ ጋር ተስማምቶ ሰውን የሚጠቅም ሆኖ ባገኘው በርሱ ከመጠቀም አልመለስም” ይላል የአቤው ምልክዓም። ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም “ከበጣም መጥፎ መጥፎ፤ ይሻላል” የሚል ፈሊጥ ነበራቸው፡፡ “ሹመት የጡረታ አበል ወይም የማባበያ ጉቦ አይደለም” የሚል አቋም ያለው ምልክዓም “በመልካም አገር ተፈጥሮ መደህየት፣ የወንጀልና የሥራ ፈትነት ብዛት፤ የሰነፍ መሪዎችና ፈራጆች የሥራ ውጤቶች ናቸው” ይላል፡፡

እንደ ሃሳባቸው ስሉጥ የሥራ መሪዎችን (ባለሥልጣናትን) ማግኘት አልቻሉም እንጂ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም አደገኛ ቦዘኔነትን ለማጥፋትና አምራች ኃይሉን ለማብዛት ጥረት ያደርጉ ነበር፡፡ በጣም የገረመኝ ጉዳይ ደግሞ የመኖሪያ ቤት ዕጥረትን ለማቃለል ምልክዓምም የተጠቀመበት ዘዴ ነው፡፡ “…1ኛ” የመንግስት ሠራተኞች ለግል ባለጥቅሞች ገባር በመሆን የኑሮ ቀንበር እንዳይከብዳቸው በማንኛውም መንገድ የኑሮአቸውን ሸክም ማቃለል አለብን፡፡ ሀ) የመንግሥት ሠራተኞች መኖሪያ ቤቶች መሥሪያ የ30 ሚሊዮን ብር በጀት ለመጀመሪያ ጊዜ መንግሥታችን መድቧል፡፡ ለ) በከተማዎቻችን ውስጥ ቤቶች እየተሰሩ ለመንግሥት ሠራተኞች ይሰጣሉ፡፡ የመንግሥት ሠራተኞችም ለቤቶቹ የሚወጣው ገንዘብ ከደሞዛቸው እየተቀነሰ እስኪመለስ ድረስ ይከፍላሉ። ሐ) ያከፋፈሉም ሁኔታ፤ ለግል ባለቤቶች መቶ ብር ኪራይ ይከፍል የነበረው ሐምሳ፤ ሐምሳ ይከፍል የነበረው ሃያ አምስት፤ በጠቅላላው ማንም ሰው ድሮ ይከፍል የነበረውን ግማሽ እየከፈለ መንግሥት ለሠራለት ቤት ያወጣውን ገንዘብ ይመልሳል፡፡ መ) ዕዳውን በረጅም ጊዜ ከፍሎ ከጨረሰ በኋላ ቤቱና ቦታው የራሱ ንብረት ሆኖ ይፀናለታል፡፡ 2ኛ. መንግሥት በአንድ በኩል ገንዘብ ሲያወጣ ባንድ በኩል ደግሞ ሠራተኞች ከሚኖሩባቸው ቤቶች የሚያገኘው ተመላሽ ገቢ ባጀቱን ሳያቋርጥ እንዲቀጥል ስለሚያደርግለት፤ ይህ ዓይነቱ ሥራ ሳያቋርጥ መቀጠል አለበት” (ገጽ 95-96) ኢህአዴግም የተጠቃሚውን ስብጥር አሰፋው እንጂ፤ በገቢር እየተረጐመው ያለው ይህንኑ የምልክዓምን ዕቅድ ነው ማለት ያስችላል፡፡ “እሱን አይደለም” ቢባል እንኳ “ተመሳሳይ ነው” ብሎ መከራከር ይቻል ይመስለኛል፡፡

ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ በስፋት እየተገነቡ የሚገኙ የጋራ መኖሪያ ህንጻዎችና የ40/60 ፕሮጀክቶች ለዚህ አሳማኝ ዋቢዎች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ የመሬት ባለቤትነትን በተመለከተም ምልክዓም የሚከተለውን አቅዶ ነበር “…የአንዳንድ ሰዎችን ቁጣ እየፈራን የሃገራችንን ጠቅላላ ጥቅም የሚጐዳ ነገርን ዝም ብለን ማየት የለብንም፡፡ 1ኛ) ለርሻ የሚሆኑ መሬቶች ሁሉ ለሀገራችን ገበሬዎች ይደለደላሉ፡፡ የጢሰኛና ገባር ታሪክም በዚህ ያበቃል፡፡ 2ኛ) በታወቀ ጊዜ በገንዘብ ሳይገዛ በልዩ ልዩ የማጭበርበር ምክንያት ብዙ የከተማ ቦታ የያዘ ከሁለት ቤቶች በላይ ያለው ሰው በቦዘን ያስቀመጠው ቦታ ቢገኝ፤ መንግሥት የቤት መሥሪያ ገንዘብ እያለው መሬት ለሌለው ሰው ይሰጣል፡፡ 3ኛ) ማንኛውም ሰው መንግሥት ሳያውቅ መሬት መግዛት፣ ሻጩም መሸጥ አይፈቀድለትም” (ገፅ 97) ሰው ከእንስሳት በታች ይታይ በነበረበት ዘመን ላይ አቤ ይህን ደፍሮ መጻፉ ያስደንቃል፡፡ ምንም እንኳ የጢሰኛና ገባርን ሥርዓት በማፈራረስ መሬትን ለአራሹ ያደረገው ደርግ ቢሆንም ኢህአዴግም ይህንኑ ሥርዓት ጠንክሮ ቀጥሎበታል፡፡ የህገወጦች የመሬት ወረራ ከቁጥጥሩ በላይ ስለሆነበትም ነባር ይዞታዎችን ሁሉ ወደ ሊዝ የሚያስገባ አዋጅ ለማውጣትም ተገዷል፡፡ “እኛ የሕዝብ ባለዕዳዎች ነን እንጂ ሕዝብ የኛ ባለዕዳ አይደለም፡፡ የተማርነውም የተሾምነውም በህዝብ ላይ ስለሆነ የሕዝብ አሸከርነታችንንና ባለዕዳ መሆናችንን ማመን አለብን” ይላል ምልክዓም፡፡ ኢህአዴግም መሠረታዊ የአሰራር ለውጥ (ቢ.ፒ.አር) እና የማህበራዊ አገልግሎት መልሶ ማዋቀር (ሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም) ለማምጣት ደፋ ቀና ሲል ነበር፡፡ ግን ሁሉም ተጨናግፎበታል፡፡

Published in ህብረተሰብ
  • ከቤተክርስቲያን ጋር ፀብ የለንም፤ ለአመፃ አልመጣንም” (“የማህበረ ዘደቂቅ ኤሊያስ” መሪዎች)
  • “በማህራችን እኔ ኤልያስ ነኝ የሚል አላጋጠመኝም”
  • “ነብዩ ኤልያስ በነገረን መንገድ የጥንቷን ሃይማኖት እያስተካከልን ነው -
  • “ቅዱስ ኤልያስ በኢትዮጵያ ሚሊኒየም ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየተዘዋወረ ነው”

ነብዩ ኤልያስ ለፍርድ ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየታየ ነው ከሚለው እምነታቸው ጋር በተያያዘ ድንጋይ ተወርውሮባቸው በተፈጠረ ሁካታ ለሰባት ቀናት ታስረው የነበሩት አባ ዮሴፍ ብርሃነ፣ አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን፣ መምህር ወልደመስቀል ፍቅረማሪያም እንዲሁም ፕሮፌሰር ይስማማው አለሙ፤ ሃይማኖታችን ተዋህዶ ነው፤ ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል አላግባብ የተጨመረ ነው ይላሉ፡፡ “ማህበረ ዘደቂቀ ኤልያስ” በሚል ስያሜ ራሳቸውን የሚጠሩት የማህበሩ መሪዎች፤ አዲስ ሃይማኖት እንዳልፈጠሩ ሲያስረዱ፣ የጥንቷን እውነተኛ ሃይማኖት ወደ ትክክለኛ ቦታዋ እንድትመለስ እያደረግን ነው ብለዋል፡፡ ይህን የምንሰራው ነብዩ ኤልያስ በነገረን መንገድ እንጂ እኛ በመሰለን መንገድ አይደለም የሚሉት የማህበሩ መሪዎች፤ በማህበሩ ውስጥ ኤልያስ ነኝ የሚል ሰው የለም ብለዋል፡፡

ከማህበሩ መሪዎች መካከል አንዱ የሆኑት አባ ዮሴፍ ብርሃነ “ኤልያስ ወደ ምድር መጥቷል” በሚለው እምነታቸው ዙሪያ ተጠይቀው፤ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ አለምን ለመፋረድ ከገነት ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየተዘዋወረ ነው ብለዋል፡፡ ኤልያስ መጥቷል ስላልን አይመጣም፡፡ እኛ ኤልያስ አልመጣም ስላልን አይቀርም ያሉት አባ ዮሴፍ፤ ኤልያስ እንደሚመጣ በመፅሃፍ ቅዱስ በግልፅ የተነገረ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን የሚመጣበት ጊዜም ስለተጠቀሰ ጊዜውን አስልቶ ማወቅ ይቻላል ብለዋል፡፡ ከአንዳንድ ሰዎች ዘንድ ተቃውሞ እንደተሰነዘረባቸው ያመኑት አባ ዮሴፍ፤ እስካሁን ጉዳዩ በሲኖዶስ ቀርቦ እንዳልተወገዘና ሲኖዶሱ ጉዳዩን ቢመረምረው እንደሚወዱ ገልፀዋል። ማህበሩን ከተቀላቀለች አንድ አመት ከ7ወር እንደሆናት የገለፀችው አርቲስት ጀማነሽ፤ አንዳንድ ሰዎች ጀማነሽ የመሠረተችው አዲስ ሃይማኖት መጥቷል በሚል ህብረተሰቡን እያደናገሩ ነው ካለች በኋላ፣ እኔ የመሠረትኩት አዲስ ሃይማኖት የለም ብላለች፡፡ “ተዋህዶ” የሚለው ስም ከጥንት የኖረ የሃይማኖታችን መገለጫ እንጂ እኔ የፈጠርኩት አይደለም ያለችው አርቲስቷ፤ “እውነትን እየተናገረ በሚኖር ሰው ላይ ክፉ ስም እየለጠፉ ለማሳደድና እውነትን ለመደበቅ ከመሞከር እውነቱን መመርመር ይሻላል” ብላለች፡፡

ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል አላግባብ የተጨመረ መሆኑን የሚያምኑት የማህበሩ መሪዎች፤ የጥንቷ እውነተኛ ሃይማኖት መገለጫዋ ተዋህዶ የሚለው ስያሜ ነው ብለዋል፡፡ “ኤልያስ መጥቷል ትላላችሁ፤ ኤልያስ በማህበራችሁ ውስጥ አለ ወይ?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ፤ “ኤልያስ መጥቷል አልመጣም የሚለው መልዕክት ሊያከራክር ቢችልም፣ እስካሁን በማህበራችን እኔ ኤልያስ ነኝ የሚል አላጋጠመኝም” ብላለች፡፡ መ/ር ወልደመስቀልም በበኩላቸው፤ በበረሃ ያሉ፤ በፆምና በፀሎት የተጉ አባቶቻችን ኤልያስ ተገልጦላቸዋል፣ ዳሷቸዋል፣ አነጋግሯቸዋል” ብለዋል፡፡ በፖሊስ የታሰሩበትን ምክንያት ተጠይቀው ሲመልሱ፣ በሚያዝያ 16 ቀን የኪዳነምህረትን ዝክር ለመዘከር 4 ኪሎ ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን አካባቢ ወደ ምትገኝ የማህበሩ መሰብሰቢያ ቤት ፀበል ፃዲቅ ይዘው በሚሄዱ አባላት ላይ አንዳንድ የሠፈሩ ወጣቶች ድንጋይ በመወርወራቸው በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በወጣቶቹ ድርጊት አንዲት ታዳጊ መፈንከቷን የገለፁት የማህበሩ መሪዎች፤ በእለቱ በከሣሽነት ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሄደው የከሳሽነት ፎርም ሞልተው ቃላቸውን ከሰጡ በኋላ፣ በጣቢያው አዛዥ ውሳኔ የከሳሽነት ቃላቸው ተቀይሮ በተከሳሽነት ቃላቸውን እንዲሰጡ መደረጋቸውን ተናግረዋል፡፡

ከከሳሽነት ወደተከሳሽነት እንዲቀየሩ የተደረገው ቀደም ሲል የአካባቢው ሰው ለፖሊስ ጣቢያው ተደጋጋሚ አቤቱታ በማቅረቡ መሆኑን መምህር ወልደመስቀል ተናግረዋል፡፡ ማህበሩ መርሃ ግብሮችን ሲያከናውን ድምጽ ይረብሸናል የሚሉ አቤቱታዎች እንደቀረቡብን ተረድተናል፣ ነገር ግን በፍርድ ቤት ሲቀርቡ በደፈናው ሁከት ፈጠራችሁ የሚል ክስ ነው የተመሰረተብን ብለዋል የማህበሩ መሪዎች፡፡ በመጀመሪያ የፍርድ ቤት ውሎ የዋስ መብታቸውን ቢጠይቁም፤ መርማሪው የአካባቢው ህብረተሰብ ቦታውን ለቀው እንዲወጡ የሚል አቤቱታ እያቀረበ ስለሆነ ጉዳዩ እስኪጣራ የዋስ መብታቸውን እቃወማለሁ በማለቱ ለ7 ቀናት በእስር መቆየታቸውን የገለፁት የማህበሩ መሪዎች፤ በመጨረሻ ግን ስትፈለጉ ትቀርባላችሁ ተብለው እያንዳንዳቸው በ500 ብር ዋስ እንደተለቀቁ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

እንዴት ሰነበታችሁሳ!

ጋብሮቮያዊው ያወጣው ማስታወቂያ እንዲህ ይላል፡፡ “በቀን ሁለት ጊዜ እንቁላል የምትጥል ዶሮ እገዛለሁ፡፡” ለእኛ ደግሞ በቀን ሁለት ጊዜ ዕንቁላል መጣሏ እንኳን ቢቀርብን ዋጋ ሲቆልሉባት አፍ አውጥታ “ይሄ ዋጋ እንኳን ለእኔ ለፍየል ወጠጤም ይበዛል…” የምትል የዶሮ ዝርያ ይስጠንማ! እኔ የምለው…በዓሉ እንዴት አከረማችሁሳ! የሁለት መቶ ብር ዶሮ፣ የሁለት ሺህ ብር በግ፣ የሃያ ሺህ ብር ሠንጋ…ግርም አይላችሁም! እንደዛም ሆኖ እስካሁን ፋሲካን ‘በተጨማሪ ሰዓት’ እያከበርን ያለን መአት ነን፡፡ የምር እኮ የበዓል መምጣትና የእኛ አከባባር ከዓመት ዓመት ‘ትራንስፎርም’ እያደረገ ‘በዋዜማውና በማግስቱ’ ያሉትን የእረፍት ጊዜያት በራሳችን ውሳኔ እያራዘምን ከጥቂት ዓመታት በኋላ “ማንኛውም በዓል ከአምስት ቀን ያላነሰ ከሳምንት ያልበለጠ የአከባበር ቀናት ይኖሩታል” የሚል አዋጅ ሊያስፈልገን ይችላል፡፡ ለክፉም ለደጉም እንኳን ለዳግማይ ትንሳኤ አደረሳችሁማ!

ስሙኝማ…ሰውየው ማለዳ ይነሳና የዞረ ድምር እያንገዳገደው ወደሚያዘወትረው ቡና ቤት ይሄዳል። አሳላፊውንም “ጓደኛዬ ትናንት ማታ እዚህ ነበር እንዴ?” ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ አስተናጋጁም “አዎ፣ እዚሁ ነበሩ…” ሲል ይመልስለታል፡፡ ይሄኔ ሰውየው ምን ብሎ ቢጠይቅ ጥሩ ነው… “እኔ አብሬው ነበርኩ?” (ከጠጡ አይቀር እንዲህ ነው!) ምን መሰላችሁ…ሰሞኑን “እኔ አብሬው ነበርኩ?” አይነት ነገር ውስጥ የገባን መአት ነን። ዘንድሮ እንደሁ ፍጹም አገርኛ ቀለም የነበራቸው በዓላት እንኳን ለዛቸው እየጠፋ የበዓል ማክበር አልፋና ኦሜጋ መጠጥ ብቻ እየሆነ ነው፡፡ ወዳጆቼ እንደነገሩኝ በዛው ልክ በተለይ በምሽት ረብሻውም እየባሰበት ነው አሉ፡፡ በነገራችን ላይ…ስለ መጠጥ ካወራን አይቀር…ወተት ጭራሽ በአልኮል እየተተካ ነው ማለት ነው? ልክ ነዋ…ብዙ የከተማው ‘ታዳጊዎች’ ስልጣኔ የጠጅ ብርሌና የድራፍት ብርጭቆ ማነቅ ሆነ! አንዳንዴ ሳስበው ምን ይመስለኛል መሰላችሁ…በቅርብ ጊዜ በህጻናት ጠጪዎች “ከዓለም አንደኛ…” ምናምን የሚል ‘የስም ጉትቻ’ ሳያስጨምርልን አይቀርም።

ግራ የሚገባኝ ነገር…አለ አይደል… ስለዚህ በጣም አሳሳቢ ጉዳይ “እኛንም በጣም አሳስቦናል፣ መፍትሄ እየፈለግን ነው…” የሚል ኦፊሴላዊ ድምፅ ምነው አንሰማሳ! እናማ…በበዓል ወቅት ተሰብስቦ በአንድ መሶብ ተሻምቶ መብላት ‘ጎጂ ባህል’ አይነት ነገር እየተደረገ…አለ አይደል… ሩጫ ሁሉ ወደ መጠጥ ቤት ብቻ ሆኗል፡፡ በዓል ጥቂት ቀናት እስኪቀሩት ጀምሮ በየ‘ሲፑ’ ቤት የምናየው ግርግር በጣም አስገራሚ ነው፡፡ እኔ የምለው እናንተ እንደልባችሁ ‘ፈረንካውን’ የምትረጩት…ገንዘቡን ለማባዛት ‘ምን አይነት ዶሮ’ ነው የሚያስፈልገን! ቂ…ቂ…ቂ… የዶሮ ነገር ካነሳን አይቀር እነኛ ጉደኞቹ ጋብሮቮዎች ምን ያደርጋሉ አሉ መሰላችሁ…ማታ፣ ማታ የዶሮ ቤቶች ያሉትን መብራቶች በሙሉ አብርተዋቸው ያድራሉ፡፡ ለምን መሰላችሁ… ዶሮዎቹ የነጋ መስሏቸው ደጋግመው እንቁላል እንዲጥሉ! እናላችሁ… የበዓል ምልክት የገባው ግርግር መሆኑ ቀርቶ የመጠጥ ቤቱ አካባቢ ግርግር ሲሆንና ጨርቅ የተሸከሙ ሰዎች ሳይሆኑ ጨርቅ የሆኑ ሰዎች ብዛት ሲሆን…አለ አይደል…የሆነ የተሳሳተ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ እግረ መንገዴን…አንዱ ሰውዬ ጓደኛውን እንዲህ ይለዋል… “አጎትህ ግን ሰክሮ ሲንገዳገድ አንድ ቀን መኪና እንዳይገጨው፡፡” ሰውየውም “እሱን መቼም ቢሆን መኪና አይገጨውም…” ሲል ይመልሳል። ሰውየው ለምን እንደዛ እንዳለ ሲጠየቀው ምን ብሎ መለሰ መሰላችሁ…“ሁልጊዜ በእጁ ትንሽ ሳጥን ይሸከማል፡፡

ሳጥኗ ላይም በትልቁ ‘ፈንጂ’ የሚል ስለተጻፈበት ማንም ደፍሮ አይገጨውም፡፡” እናላችሁ…ከበዓል አከባበር ምስቅልቅላችን ጋር… አብሮ የመብላት ባህላችን፣ አይደለም በእውን ከፈጠራ ሥራዎች እንኳን ሊጠፋ ሲቃረብ የምር ሊያሳስብ ይገባል፡፡ አንዲት ወዳጄ ያጫወተችኝን ስሙኝማ፡፡ የሆነ አሪፍ ከተማ ዳር ያለ መዝናኛ ነው፡፡ ሰውየው አሪፍ የሆነች ‘ከሦስት ቁጥር ቀጥሎ ያለው ቁጥር’ ታርጋ የተለጠፈባት ነች፡፡ ሰውየውና ሾፌሩ ከመኪናው ወርደው አንድ ጠረጴዛ ቦታ ይይዛሉ፡፡ ሹፌሩ አንገቱን እንደ ደፋ ነው፡፡ ሰውየው ለራሱ ጥብስና በቅርብ ከመጡ የቢራ ብራንዶች አንዱን ያዛል። ለሾፌሩ ለስላሳ ያዝለታል፣ ጥብሱን ጥርግ አድርጎ ይበላል፡፡ ቢራም ይደግማል፡፡ ለሾፌሩ አንድ ጊዜም “ቅመስ” ወይ “እንብላ” አላለውም- አንድ ጠረጴዛ ላይ ተቀምጠው! እንደገና ሌላ ጥብስ ያዝና ጥርግ አድርጎ ይበላል፡፡ ሦስተኛ ቢራም ያዛል፡፡ ይሄን ሁሉ ጊዜ ሾፌሩ ዓይኖቹን ጠረጴዛ ላይ እንደተከለ ነው፡፡ ሰውየው ቢራውን ሦስት አራተኛ ይጠጣና ትንሽ ትተርፋለች፡፡ ይሄኔ ምን ቢያደርግ ጥሩ ነው… ጠርሙሱን ገፋ እያደረገ ሾፌሩን “ጠጣ…” አለው፡፡ እናላችሁ…ይሄኔ ነው ምን አይነት ዘመን መጣ የምትሉት፡፡ ሾፌሩን መኪና ውስጥ ጠብቀኝ ምናምን ማለት ሲችል አጠገቡ አስቀምጦ ብቻውን ሁለት ጥብስ ጥርግ ሲያደርግ ምን አይነት ዘመን ነው! እና ወዳጄና አብረዋት የነበሩት እንደገመቱት ሰውየው የትኩስ ‘ቦተሊካ’ ተሿሚ ነገር ይታይበት ነበር፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…ተዘርዝሮ የማያልቅ መአት ችግር አለብን፡፡ ግን በዚህ ሁሉ ችግር መሀል ቢያንስ፣ ቢያንስ ያለችንን አብረን ተካፍለን መብላት እንችል ነበር፡፡ አይደለም አብሮን ያለ ሰው… ራቅ ብሎ ያለ ጠረጴዛ ላይ ያለን የማያውቁትን ሰው “እንብላ…” ማለት እኮ እዚቹ እኛ አገር የተለመደ ባህል ነበር፡፡

እናማ…ምን እየሆንን ነው! ይሄን ያህል “እኔ ከሞትኩ…” አይነት ግለኝነት በአጭር ጊዜ የወረረን ለምን እንደሆነ ተመራምረው ቁርጣችንንን የሚነግሩን የማህበረሰብ ጥናት ባለሙያዎች ያስፈልጉናል፡፡ ብዙዎቻችን ራሳችንን ከመውደዳችን የተነሳ ነገረ ሥራችን ሁሉ የጓዳ ብቻ እየሆነ ነው፡፡ ምስጢራችን እየበዛ ሲሄድ “እከሌን አብሮ አደጌ ስለሆነ አብጠርጥሬ አወቀዋለሁ…” “እከሊት እኮ ባህርዩዋን ከትምህርት ቤት ጀምሮ ነው የማወቀው…” መባባል እየናፈቀን ነው፡፡ ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…የምስጢር ነገር ካነሳን አይቀር ይቺን ክላሲክ የሆነች የምስጢር ነገር ስሙኝማ…ሰውየው ማታ ወደ አሥር ዓመቱ ገደማ የሚሆነውን ልጁን “ደህና እደር…” ለማለት ወደ መኝታ ክፍሉ ይሄዳል፡፡ ልጁ ለካ ቅዠት ውስጥ ኖሮ እየተወራጨ ይለፈልፋል፡፡ አባትየው ይቀሰቅሰውና ደህንነቱን ይጠይቀዋል፡፡ ልጁም በህልሙ አክስቱ ስትሞት ማየቱን ይነግረዋል፡፡ ሰውየውም አክስቱ እንዳልሞተች ይነግረውና ልጁም ይተኛል፡፡ በማግስቱ አክስትየው ትሞታለች፡፡ ከአንድ ሳምንት በኋላ አባት እንደገና ልጁ መኝታ ክፍል “ደህና እደር…” ሊለው ይሄዳል፡፡ ለካስ ልጁ ቅዠት ላይ ኖሮ እየተወራጨ ይለፈልፋል፡፡ አባትም ቀስቅሶ ደህንነቱን ይጠይቀዋል፡፡ ልጁም ወንድ አያቱ ሞተው በህልሙ ማየቱን ይነግረዋል፡፡ አባትየውም ወንድ አያቱ እንዳልሞቱና በህይወት እንዳሉ ነግሮት ልጁም ይተኛል፡፡ በማግስቱ ወንድ አያትየው ይሞታሉ፡፡

ከጥቂት ሳምንታት በኋላ አባት እንደገና ልጁ መኝታ ክፍል “ደህና እደር…” ሊለው ይሄዳል፡፡ ለካስ ልጁ ቅዠት ላይ ነበር፡፡ አባትም ቀስቅሶ ደህንነቱን ይጠይቀዋል፡፡ ልጁም አባቱ ሞቶ በህልሙ ማየቱን ይነግረዋል፡፡ አባትየውም እንደማይሞትና ደህና መሆኑን ነገሮት ልጁ ይተኛል፡፡ ሰውየው ወደ መኝታ ቢሄድም በጣም ከመጨነቁ የተነሳ እንቅልፍ ሊወስደው አልቻለም፡፡ በማግስቱ ሰውየው እንደሚሞት በማሰብ ፍርሀት ጠፍሮ ያዘው፡፡ ጠዋትም ከለባበሰ በኋላ እንዳይጋጭ በመፍራት መኪናውን በጣም ዝግ ብሎ እያሽከረከረ ሄደ፡፡ የምግብ መመረዝ ይገጥመኛል ብሎ በመፍራትም ምሳውን ሳይበላ ጦሙን ዋለ። የሚያውቀውን ሰው ሁሉ ሸሸ፡፡ አንዲት ድምጽ በሰማ ጊዜ ወይ በድንጋጤ ይዘላል፣ ወይ ጠረጴዛው ስር ይሸሸጋል፡፡

ከሥራ በኋላ ቤቱ ተመልሶ ሚስቱን ሲያገኛት እንዲህ ይላታል፡፡ “ዛሬ በህይወቴ በጣም አስቀያሚው ቀን ነበር…” ይላታል፡፡ እሷ ምን አለች መሰላችሁ…“አንተ እሱን ትላለህ፡፡ ወተት የሚያመላልስው ሰውዬ ዛሬ ጠዋት በራችን ላይ አይደል እንዴ ድፍት ብሎ በዛው የቀረው!” ለካስ የልጁ አባት ወተት አመላላሹ ነበር! ምስጢረኝነታችን ቀንሶ ግልጽነታችን የሚጨምርበት ዘመን ይምጣልንማ፡፡ በመሶብ ዙሪያ ተሰባስበን “በሞቴ! በሞቴ እያልኩህ!...” ”እንዲህ ቆሜማ እምቢ አትይኚም፣ ጡር አይደለም እንዴ!” እየተባባልን አብሮ የመብላት ባህላችን እንደ ጥንቱ የሚሆንበትን ይመልስልንማ! “መሶቤን ያያችሁ እስቲ ልያችሁ…” ከማለት አድኖን አብረን ተሻምተን የምንበላበትን መሶባችንን አንድዬ ይመልስልንማ! ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

በአሜሪካ፣ “serial killer” ተብሎ በፖሊስ የሚታደን ሰው…

በኛ አገር “አርበኛ” ወይም “ጀግና” ተብሎ ሊወደስ ይችላል (በአብዮቱ አመታት ሲተላለቁ እንደነበሩት አብዮተኞች)

በፈረቃ ከምትሰራበት በርገር ኪንግ እንደወጣች ጠፍታ የቀረችው አማንዳ ቤሪ፣ “ፊቷን አየሁ፤ ድምጿን ሰማሁ” የሚል ሰው ሳይገኝ 11 አመታት አልፈዋል። የጠፉ ልጆችና ልጃገረዶች፣ በሁለት ቀናት ውስጥ ተፈልገው ካልተገኙ ብዙውን ጊዜ መጨረሻቸው አሳዛኝ ነው። ተገድለው ነው የሚገኙት። ሳምንት ሙሉ ተፈልጋ ያልተገኘችው አማንዳ፣ ከዚህ ዘግናኝ ህልፈት አትተርፍም የሚል ነበር የመርማሪዎች ግምት። አስገራሚው ነገር ከሳምንት በኋላ፣ ለእናቷ አንድ የስልክ ጥሪ ደረሰ። የተደወለው ከአማንዳ ሞባይል ነው። የእናቷን ድንጋጤና ጭንቀት ልክ አልነበረውም። ስልኩን ሲያነሱት ግን፣ የልጃቸውን ድምፅ አልሰሙም። ሞታለች የሚል መርዶም አይደለም። ከአማንዳ ጋር ተጋብተን ሚስቴ ሆናለች የሚል የወንድ ድምፅ ነው የሰሙት። በኢትዮጵያዊኛ ቋንቋ ብንተረጉመው፣ “ጠልፌ ወስጃታለሁ፤ ጠልፌ አግብቻታለሁ” እንደማለት ነው። በቃ፣ ስልኩ ተዘጋ።

የአማንዳ እናት መረጃውን ለፖሊስ ቢያደርሱም፣ የፖሊስ ምርመራና ፍለጋ ባይቋረጥም፣ ውጤት አልተገኘም። ከአመት በፊትም፣ ከዚያው አካባቢ አንዲት ወጣት ሴት ጠፍታለች። ከአማንዳ በኋላም እንዲሁ፣ ከተመሳሳይ ቦታ ሌላ የ14 አመት ሴት እንደወጣች ቀርታለች። የት ይግቡ፣ የት ይድረሱ ፍንጭ አልተገኘም። በእርግጥ አንዲት ጠንቋይ በቴሌቪዥን ስርጭት አማንዳ ህይወቷ አልፎ አስከሬኗ ጥልቅ ባህር ውስጥ ሰጥሟል ብላ እንደተናገረችውም አልሆነም። ሶስቱ ሴቶች ከነሕይወታቸው ከአስር አመት በላይ ሲሰቃዩ የኖሩት፣ አማንዳ ከጠፋችበት አካባቢ ብዙም የማይርቅ መኖሪያ ቤት ውስጥ ነው - በሶስት በአራት ኪሎሜትር ርቀት። በኤርየል ካስትሮ ተጠልፈው ከታገቱበት እለት ጀምሮ፣ ሶስቱ ሴቶች ከቀን ቀን፣ ከአመት አመት፣ ቤት እንደተዘጋባቸው መከራ ይበላሉ።

ለመውጣት ቢሞክሩ፣ ድብደባውና እርግጫው! አሁንም በኢትዮጵያዊኛ ቋንቋ እንግለፀው ከተባለ፣ “ከቤት ንቅንቅ ብትይ እግርሽን እሰብረዋለሁ” እያለ ሚስቱን ነጋ ጠባ የሚያሰቃይ ባል እንደማለት ነው። እንዴት ብትሉ፤ ከሁለት ሳምንት በፊት ኢቲቪ በሁለት ክፍል ካቀረበው ድራማ መልሱን ማግኘት ይቻላል። “ጠልፎ ማግባት” በህግ የተከለከለ የወንጀል ድርጊት መሆኑን ለማሳየትና፣ “ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለማስጨበጥ” ታስቦ የተሰራ ድራማ ነው። እንግዲህ አስቡት። “ጠልፎ ማግባት” ብዙም እንደ ወንጀል ስለማይቆጠር፣ “በሽማግሌና በእርቅ” ሊያልቅ የሚችል ቀላል ጉዳይ እንደሆነ ተደርጎ ስለሚታሰብ… ያን ያህልም “ጉድ! ጉድ! አቤት ጭካኔ!” የሚያሰኝ አይደለም ማለት ነው። እናም፤ “ጠለፋ ወንጀል ነው” እያሉ “በድራማ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ጥረት ማድረግ” አስፈለገ። ገና እዚህ ደረጃ ላይ ነን ያለነው። ከኢትዮጵያውያን መካከል ግማሾቹ፣ ባል ሚስቱን የመደብደብ መብት አለው ብለው እንደሚያምኑም ባለፉት አስር አመታት የተካሄዱ ሶስት ተከታታይ ጥናቶች ያረጋግጣሉ።

በአጭሩ፣ ጠልፎ ማግባትና ማሰቃየት፣ ብዙ ጣጣ የለውም። ድብቅነትን አይጠይቅም። በአሜሪካ ግን፣ ጣጣው ብዙ ነው። ጠልፎ ማግባት ይቅርና፣ ሚስትን “የት ወጣሽ የት ገባሽ” እያሉ ማሰቃየት እንደ ተራ ነገር አይቆጠርም። በዝምታ የሚታለፍ ቢሆን ኖሮማ፣ ኤርየል ካስትሮ ከመጀመሪያ ሚስቱ ጋር ባልተለያየ ነበር። የኤርየል ቤትና የሚስቱ ወላጆች ቤት ቅርብ ለቅርብ ቢሆንም፣ እየመጡ እንዲጠይቋት ወይም እየሄደች እንድትጠይቃቸው አይፈልግም ነበር። አንዳንዴ እሱ በማይኖርበት ሰዓት እህቷ ልትጠይቃት ስትመጣ እንኳ፣ በሩ ስለሚቆለፍ መግባት አትችልም። ኤርየል፣ ሚስቱን ቤት ውስጥ ቆልፎባት ነው የሚሄደው። ከዚያም ድብደባ ተጨመረበት። አንዴ አፍንጫዋን ሰብሯታል። ሚስቱን በመደብደቡ ሁለቴ የታሰረው ኤርየል፣ ባህሪውን ሊያሻሽል ስላልቻለ ሚስት በፍቺ ጥላው ወጣች - በፖሊስ ታጅባ። “ሚስቱን ቢደበድብ መብቱ ነው” የሚል አይነት አስተሳሰብ በስፋት የሌለበት አገር ውስጥ፣ “ውልፊት ትይና እግርሽን እሰባብረዋለሁ” እያለ እድሜ ልክ ሚስቱን እያሰቃየ መኖር አይቻልም - ማንም እንዳያውቅ ደብቆ ካላሰቃየ በቀር። ኤርየልም፣ ይህንኑን ነው ያደረገው - ጠልፎ እየወሰደ በድብቅ ማሰቃየት።

እንደ ኢትዮጵያ በመሳሰሉ አገራት፣ በሃይማኖትና በብሄረሰብ ስም፣ በአገርና በህዝብ ስም፣ ሰውን የማጥቃትና የማሰር፣ የማሰቃየትና የመግደል… ቅስቀሳዎች ወይም ዘመቻዎች በየጊዜው በግላጭ ይፈፀሙ የለ? ይህንን የሚፈፅሙ ክፉ ሰዎች፣ ለጭካኔያቸው ሰበብና ማመካኛ አያጡም። እንዲያውም፣ “አገር ወዳድ አርበኛ፣ ቆራጥ አብዮተኛ፣ የቁርጥ ቀን ጀግና”… የሚል ውዳሴ ይጎርፍላቸዋል። ስቃይና ግድያ የሚፈፅሙትም በግላጭ ነው። እንደ አሜሪካ በመሳሰሉ በስልጣኔ ደህና የተራመዱ አገራት ውስጥ ግን፣ ሰውን በግላጭ ለማሰቃየትና ለመግደል የሚያስችል ሰበብና ማመካኛ ማግኘት ከባድ ነው። ክፉ ሰዎች፣ በግላጭ እንዳሻቸው ጭካኔ እየፈፀሙ በየአደባባዩ መፈንጨት አይችሉም። በድብቅ ስቃይና ግድያ ለመፈፀም የሚሞክሩ ግን አይጠፉም - ለምሳሌ ልማደኛ ነፍሰ ገዳዮች (serial killers)። ልዩነቱን አያችሁት። በኋላ ቀር አገራት ውስጥ፣ ክፉ ሰዎች ለጭካኔያቸው ብዙ አይነት ማመካኛ ማቅረብ ስለሚችሉ፣ በአደባባይ ሰውን እያሰቃዩና እየገደሉም፣ እንደ ጀግና ወይም እንደ አርበኛ ይታያሉ። በስልጣኔ ደህና የተራመዱ አገራት ውስጥ ግን፣ ክፉ ሰዎች “ልማደኛ ነፍሰ ገዳይነታቸውን” የሚሸፋፍኑበት እድል ስለሌላቸው በፖሊስ ይታደናሉ። እንደ ኢትዮጵያ በመሳሰሉ አገራት፣ “ልማደኛ ነፍሰ ገዳዮች (serial killers) የሌሉ ይመስለናል። በሌላ ስም ስለምንጠራቸው ነው - አርበኛ፣ አብዮተኛ፣ ጀግና እየተባሉ ይጠራሉ። እንደ ኤርየል ካስትሮ፣ በድብቅ የእገታና የማሰቃየት ጭካኔ የሚፈፅሙ ሰዎች በአገራችንና በሌሎች ኋላቀር አገራት የሌሉ ከመሰለ ንም ተሞኝተናል። ሞልተዋል። ግን፣ ጭካኔያቸውን ያን ያህልም መደበቅ አያስፈልጋቸውም። ሳልፈቅድልሽ ከቤት ወጥተሻል ብሎ ሚስቱን ቢደበድብ ብዙም ችግር አይገጥመውማ።

Published in ህብረተሰብ

እስከ 2004 ዓ.ም የተያዙ ህገወጥ ቦታዎች ካርታ ይሰጣቸዋል ተብሏል፡፡ በእድሮች የተያዙና ሊዝ ይከፈልባቸዋል የተባሉ ሰፊ ቦታዎች በመንግስት ስም ይሆናሉ ባለፉት አስር አመታት በሺ የሚቆጠሩ የህገወጥ ይዞታ ግንባታዎችና የ “ጨረቃ ቤቶች” በየጊዜው እንዲፈርሱ ቢደረግም፣ ለህገወጥ ይዞታዎች ካርታ ለመስጠት የሚፈቅድ መመሪያ ለሶስተኛ ጊዜ ማዘጋጀቱን የአዲስ አበባ መስተዳድር ሰሞኑን ገለፁ፡፡ ካሁን በፊት “የህገወጥ ይዞታዎችን ጉዳይ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመዝጋት ያስችላሉ የተባሉ ሁለት መመሪያዎች ወጥተው እንደነበሩ የሚታወስ ሲሆን፣ በዚህም ለ51ሺ ቤቶች የህጋዊነት ካርታ እንደተሰጣቸው የከተማዋ የመሬት ልማት አስተዳደር ቢሮ ገልጿል፡፡ የመጀመሪያው መመሪያ እስከ 1998 ዓ.ም ያለ ህጋዊ ሰነድ ለተያዙ ቦታዎች ካርታ ለመስጠት የሚፈቅድ ሲሆን፣ ከዚያ በኋላ የተያዙ ቦታዎችና የተገነቡ ቤቶች ግን ሁሉም እንዲፈርሱ የሚያስገድድ ነበር፡፡

መመሪያው እንደገና ተሻሽሎ እስከ 1994 ዓ.ም የተያዙ ህገወጥ ቦታዎችንም እንዲያስተናግድ መደረጉ ይታወሳል፡፡ ለመኖሪያ ቤት የሚውሉ ቦታዎችን በህጋዊ መንገድ ለማግኘት አስቸጋሪ በሆነባትና ከፍተኛ የመኖሪያ ቤት እጥረት በሚያጎሳቁላት ከተማ ውስጥ፤ ህገወጥ የቦታ ይዞታዎችንና ግንባታዎችን ያስቆማሉ ተብለው የወጡት መመሪያዎች የተነገረላቸውን ውጤት አላስገኙም፡፡ የጨረቃ ቤት፣ የጊዜያዊ ውል ይዞታ፣ ህገወጥ ግንባታ የሚባሉ ነገሮችን በወጉ ለይቶ ማወቅ እስከሚያስቸግር ድረስ እየተበራከተ መምጣቱና የነዋሪዎች አቤቱታ ከአቅም በላይ መባባሱ ይታወቃል፡፡ አሁን የተዘጋጀው መመሪያም ህገወጥ ይዞታዎችን ለዘለቄታው ለማስተካከል የታሰበ እንደሆነ ቢሮው ጠቅሶ፣ ያሉት ይዞታዎች የሚስተናገዱበት እንደሆነ ይገልፃል፡፡ ለመኖሪያ አገልግሎት የተያዙት እስከ 500 ካሬ ሜትር ድረስ የሆኑ ቦታዎች በነባር ስሪት ተፈቅዶላቸው የይዞታ ማረጋገጫ ካርታ እንዲሰጣቸው መመሪያው ያዛል፡፡

መመሪያው ከሚዳስሳቸው ሌሎች ጉዳዮች መካከል፣ ከ1967 ዓ.ም በኋላ በግለሰቦች ተገንብተው ኪራይ የሚያስከፍልባቸው ቤቶችን የሚመለከት ነው፡፡ ግለሰቦቹ በህግ ቤቱን ተረክበው ለባለመብቶች የይዞታ ማረጋገጫ ሰነድ በስማቸው እንደሚሰጥ መመያው ይገልፃል፡፡ በመንግስት ከተወረሱ በኋላ በፍርድ ቤት ለባለቤቶቹ እንዲመለሱ የተወሰነላቸው ቤቶችም የአፈፃፀም ችግር እንደነበረባቸው መመሪያው ጠቅሶ፤ ባለቤቶቹ ቀርበው እንዲረከቡ ይፈቅዳል፡፡ የመንግስት ቤት ባለበት ግቢ ውስጥ በግለሰቦች የተገነቡ ቤቶች ግን ህጋዊ እውቅና አያገኙም ተብሏል፡፡ እስካሁን ካርታ የተሰጣቸው ካሉም ይሰረዝባቸዋል ይላል መመሪያው፡፡

ነዳጅ ማደያዎችን በተመለከተም ከንጉሱ ዘመን አንስቶ በስራ ላይ ያሉ የነዳጅ ጣቢያዎች፣ የኪራይ ውል ዘመናቸው የተጠናቀቀ መሆኑን ቢሮው ገልፆ፣ በቦታው ላይ የተገነባው የግል ንብረት እንደማይወረስና መሬቱን በሊዝ መነሻ ዋጋ አዲስ ውል በመዋዋል ለኩባንያዎቹ እንደሚፈቀድ መመሪያው ያወሳል፡፡ በእድር ስለተያዙና ቋሚ ግንባታ ያለባቸው የመሬት ይዞታዎችን በተመለከተ የይዞታ ማረጋገጫ ሠነዳቸው በወረዳው መስተዳድር ስም እንዲሆንና በሊዝ መነሻ ዋጋ እንደተያዙ ተቆጥረው እንዲስተናገዱ መመሪያው ያዝዛል፡፡ ይሁን እንጂ፣ የእድሮች ይዞታ በሊዝ መሆኑና በወረዳ መስተዳድር ስም እንዲሆን መደረጉ ተቃውሞ ሊያስነሣ እንደሚችል የመሬት አስተዳደር ቢሮ አልካደም፡፡ በረቂቅ መመሪያው እንደተመለከተው፤ ህገወጥ ተብለው የነበሩ ይዞታዎች የህጋዊነት ሰነድ ማረጋገጫ ካርታ የሚሰጣቸው የከተማውን ፕላን የማያፋልሱ ሆነው ከተገኙ ሲሆን ችግር ያለባቸው ሆነው ከተገኙም ምትክ ቦታ በመስጠት ተስተካክለው እንዲሰሩ ይደረጋል ተብሏል፡፡

Published in ዜና

በኢትዮጵያ በተለያዩ አካባቢዎች እየደረሱ ላሉት ህገ ወጥ የዜጐች መፈናቀል መንግስት ራሱን ከተጠያቂነት ለማዳን የሚያደርገው ሙከራ “ተጨፈኑ ላሙኛችሁ” አይነት ማታለል ነው ሲል የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክራሲያዊ አንድነት መድረክ አስታወቀ፡፡ መድረክ ሠሞኑን ባወጣው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ የፌደራልም ሆነ የበታች አስተዳደሮች የአንድ መንግስት አካላት እንደሆኑና በትስስር እንደሚሠሩ እየታወቀ ዜጐች በህገ-ወጥ መንገድ ሲፈናቀሉ በክልል፣ በዞንና በወረዳ አስተዳደር አካላት ላይ ማላከክ ከተጠያቂነት እንደማያድነው አስምሮበታል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማሪያም ደሣለኝ በቅርቡ በፓርላማ ባቀረቡት ሪፖርት “ህገ-ወጡን የማፈናቀል እርምጃ የወሠዱት በሙስና የተጨማለቁ የበታች ሀላፊዎች ናቸው” በማለት የቤኒሻንጉል ተፈናቃዮችን አስመልክተው የተናገሩት ንግግር መንግስታቸውን ከተጠያቂነት ለማዳን ያደረጉት ማፈግፈግ ነው ብሏል መድረክ፡፡

“ባለፉት 21 ዓመታት በኢህአዴግ ሥርዓት በታየው የአሠራር ልምድ የበላይና የበታች የአስተዳደር አካላት በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ይገናኛሉ” ያለው መድረክ፤ የበታች አካላትም ያለ በላይ አካላት እውቅና እንዲህ አይነት ከባድ ህገ-ወጥ እርምጃ ሊወስዱ እንደማይችሉና ከዚህም በፊት የወሠዱበት ሁኔታ አለመኖሩን በአፅንኦት ገልጿል፡፡ መድረክ አክሎም፤ መንግስት ራሱን ከተጠያቂነት ለማግለል የሚያደርገውን ትግል አቁሞ ከዚህ ቀደም በጉራ ፋርዳ፣ በኦሮሚያ፣ በጋምቤላና በቅርቡም በቤኒሻንጉል ለተፈፀሙት ህገ-ወጥ የዜጐች መፈናቀሎች ሀላፊነትና ተጠያቂነቱን መውሠድ አለበት ብሏል፡፡ ዜጐችን ከሚኖሩበት አካባቢ ማፈናቀል ህገ-ወጥ ከመሆኑም በላይ በህገ-መንግስቱ ላይ የሠፈረውንና ሀገራችን የተቀበለቻቸውን የዜጐች በነፃነት መንቀሣቀስና መኖሪያ ቦታ የመምረጥ ዓለም አቀፍ ድንጋጌዎችን የሚጥስ በመሆኑ መድረክ ድርጊቱን እንደሚያወግዘው በመግለጫው አስቀምጧል፡፡

መድረክ በመግለጫው፤ “የዜጐችን እንቅስቃሴ የመቆጣጠሪያና መግቻ ሥልት ነው” ያለውን የአንድ ለአምስት አደረጃጀትንም አውግዟል፡፡ እንዲህ አይነት ህገ-ወጥ የማፈናቀል እርምጃ ለወደፊቱ በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች እንዳይፈፀም መንግስት እርምጃ በመውሠድ የዜጐችን መብት ማክበር እንዳለበት የጠየቀው መድረክ፤ በከተሞች በአዲስ አበባ አካባቢ በቦሌ ቡልቡላና በላፍቶ፣ በትግራይ ክልል በመሆኒ፣ በአላማጣ እና በመሣሠሉት አካባቢዎች በልማት ስም የሚፈፀመው ድንገተኛ የቤት ማፍረስ ዘመቻም መቆም እንዳለበት አስታውቋል፡፡ በልማት ስም ዜጐችን እያፈናቀሉ ለውጭ አገር ኢንቨስተሮች መሬት መስጠት የዜግነትን መብት የሚጥስና ክብረ-ነክ በመሆኑ ሊታረምና እርምጃ ሊወሠድበት ይገባል ብሏል መድረክ በመግለጫው፡፡ “ከቤኒሻንጉል የተፈናቀሉት ዜጐች ወደ ቤታቸው ተመልሠዋል ቢባልም አውላላ ሜዳ ላይ ስለመውደቃቸው መረጃ አለ” ያለው መድረክ፤ ዜጐች ወደ ቦታቸው ተመልሠው እንዲኖሩ መሬት ከመስጠት ጀምሮ አስፈላጊው ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጠይቆ፣ ይህንን ህገ-ወጥ ድርጊት የፈፀሙት ሀላፊዎች ለፍርድ እንዲቀርቡ በማድረግ መንግስት ይህንኑ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ እንዲያሣውቅ በመግለጫው አሳስቧል፡፡

Published in ዜና

ባለ 5 ኮከቡ ካፒታል ሆቴልና ስፓ ትናንት ተመርቆ አገልግሎት ጀመረ፡፡ በ172 ሚሊየን ብር የተሠራው ሆቴሉ 114 የመኝታ ክፍሎች አሉት፡፡ በአቶ የማነ ገ/ሥላሴ ባለቤትነት የተገነባው ይኼ የግል ሆቴል መዋኛ፣ የሴቶችና የወንዶች መታሻ ክፍሎችና መዋቢያ፣ አንድ ፎቅ ጂምናዚየም፣ ባር፣ ላውንጅ፣ የስብሰባ አዳራሾች አሉት፡፡ ግንባታው አምስት ዓመት የፈጀው ሆቴል፤ በማስፋፊያው ባለ 11 ፎቅ ሕንፃ እያስገነባ ሲሆን ከምድር በታች ሁለት ፎቅ የመኪና ማቆሚያ አለው፡፡

ሆቴሉ በአሁኑ ወቅት ለ225 ዜጐች የሥራ ዕድል የፈጠረ ሲሆን የሠራተኞቹን ቁጥር 270 የማድረስ ዕቅድ አለው፡፡ አቶ የማነ ገ/ሥላሴ የሆሲ ትሬዲንግ ሃውስ ባለቤት ሲሆኑ ድርጅታቸው አሉ ከሚባሉት የገቢና ወጪ ንግድ ድርጅቶች አንዱ ነው፡፡ ሆሲ በብረታ ብረት ማሽኖች፣ መሳሪያዎችና ሌሎች ተዛማጅ ንግዶች ላይ የተሰማራ ሲሆን፤ የእርሻ ምርት ውጤቶችንም ለውጭ ገበያዎች በማቅረብ ይታወቃል፡፡

Published in ዜና
Page 10 of 14