Saturday, 31 May 2014 14:33

ከሞት ጋር ድርድር

(ተውኔቱ የሚካሄደው የናት አኬርማን ባለ ሁለት ፎቅ መኖሪያ ቤት ውስጥ ነው፡፡ መጋረጃው ከግድግዳው ጥግ እስከ ጥግ ተንጠልጥሏል፡፡ ትልቅ አልጋና የመልበሻ ጠረጴዛ ይታያል፡፡ ግድግዳው ላይ  የተለያዩ ስዕሎችና እምብዛም ማራኪ ያልሆነ የነፋስ ግፊት (ባሮ ሜትር) ተንጠልጥሏል፡፡ መጋረጃው ሲገለጥ ለስለስ ያለ ሙዚቃ ይንቆረቆራል፡፡ መላጣው እና ቦርጫሙ የ57 ዓመቱ ቀሚስ አምራች ናት አኬርማን፣ አልጋው ላይ ተጋድሞ ጋዜጣ ያነባል፡፡ ጊዜው እኩለ ሌሊት አቅራቢያ ነው፡፡ ድንገት ኮሽታ ይሰማል፤ ናት ከመቅፅበት ከተኛበት ተነስቶ ቁጭ ይልና ወደ መስኮቱ ትክ ብሎ ይመለከታል፡፡)
ናት፡ ምንድን ነው የማየው?
(ጥቁር ኮፍያ ያደረገ አስፈሪ ፍጡር ይታያል። ከሰውነቱ ጋር የተጣበቀ የሚመስል ጥቁር ልብስ ለብሷል፡፡ ኮፍያው አናቱን ሸፍኖታል፤ ፍፁም ነጭ የሆነ ፊቱ ግን ተጋልጦ ይታያል፡፡ የሰውየው ቁመናና መላ ገፅታው ናትን ይመስላል፡፡ ቁና ቁና እየተነፈሰ የመስኮቱን ደፍ ዘልሎ፣ ክፍሉ ውስጥ ዱብ ይላል፡፡)
ሞት፡ በኢየሱስ ስም! አንገቴ ተሰብሮ ነበር እኮ!
ናት፡ (ግራ በመጋባት እያየው) አንተ ማን ነህ?
ሞት፡ ዘና ብሎ ሞት ነኝ፡፡
ናት ፡ ማን?
ሞት፡ ሞት ነኝ፡፡ ስማኝ ይልቅ…ትንሽ ቁጭ ልበል? አንገቴን ልሰብረው ነበር‘ኮ፡፡ እንደ ቅጠል እየተርገፈገፍኩ ነው የወረድኩት፡፡
ናት ፡ (ግራ እንደተጋባ) ማን ነህ ግን አንተ?
ሞት፡ ሞት ነኝ አልኩህ እኮ! እስቲ ውሃ አጠጣኝ?
ናት ፡ ሞት ነኝ? ምን ማለት ነው ሞት ነኝ ማለት?
ሞት፡ ያምሃል እንዴ? ጥቁር ልብሴና ነጭ ፊቴ አይታይህም?
ናት ፡ ይታየኛል፡፡
ሞት፡ ቆይ ዛሬ የቅዱሳን ዝክረ በዓል (ሀሎዊን) ነው እንዴ?
ናት ፡ ኧረ ይደለም፡፡
ሞት፡ ስለዚህ ሞት ነኝ ማለት ነው፡፡ እሺ አሁንስ ውሃውን አትሰጠኝም? ለስላሳም ቢሆን ግዴለኝም፡፡
ናት ፡ እየቀለድክ ነው አይደል?
ሞት፡ የምን ቀልድ ነው? ዕድሜህ - ሃምሳ ሰባት፣ ስምህ ናት አኬርማን፣ የቤት ቁጥርህ…አንድ መቶ አስራ ስምንት አይደል? መቼም እንዳልተሳሳትኩ እርግጠኛ ነኝ …የታለ ያ የመጥሪያ ወረቀት? (ከኪሱ ውስጥ አድራሻ የተጻፈበት ወረቀት አወጣና አረገገጠ፡፡)
ናት ፡ እሺ ከእኔ ምንድን ነው የምትፈልገው?
ሞት፡ ምን የምፈልግ ይመስልሃል?
ናት፡ አትቀልድ ሰውዬ! እኔ ፍፁም ጤናማ ሰው ነኝ፡፡
ሞት፡ (በመሰልቸት ስሜት) ምን ታደርገዋለህ እንግዲህ፡፡ (ዙሪያ ገባውን እየቃኘ) በጣም ደስ የሚል ቤት አለህ፡፡ ራስህ ነህ ያበጃጀኸው?
ናት፡   አይ፤ ለባለሙያ ከፍለን ነው ያሠራነው፤ ግን አግዘናታል!
ሞት፡  (ግድግዳው ላይ ያለውን ስዕል እያየ) ትልልቅ ዐይኖች ያላቸው ሕጻናት እንዴት እንደምወድ…
ናት፡   እኔ ግን አሁን መሄድ አልፈልግም፤ ገና ነኝ፡፡
ሞት፡   መሄድ አትፈልግም? በናትህ ክርክር እንዳትጀምረኝ፡፡ መውጣት መውረዱ ራሱ እንዴት እንዳጥወለወለኝ አልነግርህም!
ናት፡    የምን መውጣት መውረድ?
ሞት፡    አሸንዳው ላይ ተንጠላጥዬ ነበር፡፡ ወደ ቤትህ በተለየ መንገድ ለመግባት ነበር ያሰብኩት። እንቅልፍ እንዳልወሰደህ ሳይ ሃሳቤን ለመተግበር ወሰንኩ፡፡ እላይ ወጥቼ አለ አይደል…ድንገት ዱብ ልል ፈልጌ ነበር፡፡ ምን ዋጋ አለው፤ የሆነ ሀረግ ነገር እግሬን አስሮ ያዘኝ፤ አሸንዳውም ተሰበረ፤ አንዲት ሰበዝ ብቻ ናት አንጠልጥላ የያዘችኝ፡፡ ከዚያ ኮፍያዬም መቀደድ ጀመረ፡፡ አሁን እሱን ተወው በቃ! ይልቅ ተነሳና እንሂድ!
ናት፡  አሸንዳዬን ሰበርከው ማለት ነው?
ሞት፡  አልተሰበረም‘ኮ፡፡ አጠፍ ነው ያለው። አንተ ግን ስፈጠፈጥ ግን ምንም ድምፅ አልተሰማህም?
ናት፡   እያነበብኩ ነበር…
ሞት፡  በጣም ተመስጠህ ነበር ማለት ነው፡፡ (ናት እያነበበው የነበረውን ጋዜጣ አንስቶ ይመለከታል) “አደንዛዥ ዕፅ በቡድን ሲያጨሱ የነበሩ ተማሪዎች ጋማ ተባሉ” እስቲ አውሰኝ?
ናት፡  ገና አንብቤ አ ልጨረስኩም፡፡     
ሞት፡   እ…እንዴት ብዬ እንደምነግርህ አላውቅም፤ ጓደኛዬ አንተኮ…
ናት፡   ቆይ ለምንድን ነው በስነ ስርዓቱ የበሩን ደወል ያልደወልከው? በህገ ወጥ መንገድ መግባቱ ለምን አስፈለገ?
ሞት፡   እየነገርኩህ፤ እንደዛ ማድረግ እችል ነበር እኮ! ግን ሰርፕራይዝ ላደርግህ ፈልጌ ነው፡፡ አየህ በዚህኛው መንገድ የሆነ ድራማ ነገር አለው፡፡ “ፎውስት”ን አንብበሃል?
ናት፡    ምን?
ሞት፡   ቆይ እሺ ከእንግዶች ጋር ብትሆን ኖሮስ? እዚህ አንተ ከትልልቅ ሰዎች ጋር ቁጭ ብለሃል እንበል፡፡ እኔ ደግሞ ሞት ነኝ…የበር ደወል ደውዬ እየተንከራፈፍኩ ልግባልህ? እንዴት እንዴት ነው የምታስበው?
ናት፡    ስማ ሰውዬ፤ በጣም መሽቶብሃል
ሞት፡   ልክ ነህ፡፡ ተነሳ እንሂዳ?
ናት፡  የት ነው የምሄደው?
ሞት፡    ወደ ሞት ነዋ! እዚያ…ወንዞቹ ወተት፤ ድንጋዮቹ ዳቦ ወደሆኑበት፡፡ ታውቃለህ፤ (ጉልበቱን እያየ) በጣም ነው የቆሰለው፡፡ ገና በመጀመሪያ ሥራዬ ጋንግሪን ሳይዘኝ አይቀርም፡፡
ናት፡   እኔ ትንሽ ጊዜ እፈልጋለሁ፡፡ አሁን ለመሄድ ዝግጁ አይደለሁም፡፡  
ሞት፡   በጣም አዝናለሁ፡፡ ምንም ልረዳህ አልችልም፡፡ በቃ ጊዜው ደርሷል፡፡
ናት፡   እንዴት ነው ጊዜው የደረሰው? ከሞዲስት ኦሪጂናልስ (ቀሚስ አምራች ድርጅት) ጋር ሽርክና የገባሁት አሁን አይደል እንዴ?
ሞት፡  የተወሰነ ተጨማሪ ገንዘብ መጣ ቀረ …ምን ለውጥ አለው ብለህ ነው?
ናት፡    አንተን ይመለከትሃል?
ሞት፡   አሁን እሺ ትሄዳለህ አትሄድም?
ናት፡    (በአትኩሮት እያየው) በጣም አዝናለሁ፤ ሞት መሆንህን አምኜ ለመቀበል አቅቶኛል፡፡
ሞት፡   ምን? ማንን ጠብቀህ ነበር…ሮክ ሃድሰንን? (ሮክ ሃድሰን በኤድስ የሞተ አሜሪካዊ አክተር ነው)
ናት፡    አይ፤ እንደዚያ አይደለም፡፡
ሞት፡   ያልጠበከው ዓይነት ሞት ከሆንኩብህ ይቅርታ፡፡
ናት፡  ለምን እንደሆነ አላውቅም፤ ሁልጊዜ በሀሳቤ …ረጅም ሆነህ ነበር የምትታየኝ…  
ሞት፡ ሜትር ከሰባ ነኝ፡፡ ከክብደቴ ጋር ተመጣጣኝ ነው፡፡
ናት፡    እኔን ትመስላለህ ልበል?
ሞት፡   እና ማንን ልምሰል? ያንተ ሞት ነኝ‘ኮ!
ናት፡   እሺ በቃ ትንሽ ጊዜ ስጠኝ፡፡ የአንድ ቀን ጊዜ እፈልጋለሁ፡፡
 ሞት፡  እሺ እንድልህ ነው? አልችልም!
 ናት፡   አንድ ተጨማሪ ቀን፡፡ ሃያ አራት ሰዓት ብቻ!
ሞት፡   ምን ትሠራበታለህ? ሬዲዮው ነገ ዝናባማ ቀን እንደሚሆን ተናግሯል፡፡
ናት፡    ቆይ ቼዝ ትችላለህ?
ሞት፡   አይ፤ አልችልም፡፡
ናት፡  ፎቶ ላይ ግን ቼዝ ስትጫወት ያየሁ መሰለኝ፡፡
ሞት፡ ተሳስተሃል እኔ ቼዝ መጫወት አልችልበትም፡፡ ባይሆን ካርታ ጨዋታ እችላለሁ፡፡
ናት፡     ካርታ ትችላለህ?
ሞት፡   መጠየቁስ!
ናት፡    በደንብ ትችላለሃ?
ሞት፡   አሳምሬ!
ናት፡    ምን ለማድረግ እንዳሰብኩ ልንገርህ…
ሞት፡ ከእኔ ጋር ምንም ዓይነት ድርድር ለማድረግ ግን እንዳታስብ!
ናት፡  ካርታ እንጫወትና አንተ ካሸነፍከኝ ወዲያውኑ ተነስተን እንሄዳለን፡፡ እኔ ካሸነፍኩ ግን ትንሽ ጊዜ ትሰጠኛለህ፡፡ የአንድ ቀን ጊዜ!
ሞት፡    እስቲ አሁን በየትኛው ጊዜ ነው ካርታ የምንጫወተው?
ናት፡   ግዴለህም፡፡ በደንብ የምትችል ከሆነ እንጫወት፡፡
ሞት፡    ግን ከአንድ ጨዋታ ……
ናት፡    በእኔ ይሁንብህ… ፈታ በል፡፡ ለግማሽ ሰዓት ያህል እንጫወት፡፡
ሞት፡   ግዴለህም ይቅርብኝ፡፡
ናት፡    ይሄው ካርታው… ለምን ታካብዳለህ?
ሞት፡    እሺ ይሁን… ትንሽ እንጫወትና… ለነገሩ እኔንም ዘና ያደርገኛል
ናት፡   (ካርታ፣ ማስታወሻ ደብተርና እርሳስ እያመጣ) ግዴለህም ምንም አትቆጭበትም!
ሞት፡   ባክህ ጅንጀናህን ተወኝ፡፡ ካርዱን አምጣውና ለስላሳ ነገር ስጠኝ፤ እሚበላ ነገርም አምጣ፡፡ ኧረ በእግዚአብሔር… እንግዳ ሲመጣ የምታቀርበው ቺፕስ ምናምን እንኳን  የለህም?
ናት፡    ታች ቤት ከረሜላዎች አሉኝ፡፡
ሞት፡   ከረሜላ? ቆይ ድንገት ፕሬዚዳንቱ ቢመጡስ… ከረሜላ ልትሰጣቸው ነው?
ናት፡   አንተ ፕሬዚዳንቱ አይደለህማ!
ሞት፡  ና እሺ ጀምር…
ናት፡   ጨዋታው እንዲያምር በሳንቲም ቢሆንስ?
ሞት፡  አሁን አያምርም?
ናት፡   በሳንቲም ሲሆን የተሻለ ስለምጫወት ነው፡፡
ሞት፡   እንዳልክ ይሁንልህ፤ ኔውት፡፡
ናት፡    ናት ነው ስሜ፡፡ ናት አኬርማን፡፡ ስሜን ሳታውቅ ነው እንዴ…?
ሞት፡   ኔውት…ናት…ባክህ ተወኝ…ራሴን አሞኛል።
ናት፡    አምስት ቁጥርን ትፈልገዋለህ?
ሞት፡   አይ፡፡  
ናት፡   እና ሳብ እንጂ፡፡
ሞት፡  (እየሳበ እያለ በእጁ ያሉትን ካርታዎች እያየ) በኢየሱስ ስም፤ ምንም የረባ ነገር የለኝም፡፡
ናት፡   ቆይ ግን ምን ይመስላል?
ሞት፡  ምኑ?
 (ከዚህ ቀጥሎ ብዙ ካርታ ያነሳሉ፤ ይጥላሉ)
ናት፡   ሞት?
ሞት፡   ምን እንዲመስል ትፈልጋለህ? በቃ ጋደም ማለት ብቻ ነው!
ናት፡    ከዚያ በኋላስ ምን አለ?
ሞት፡  አሃ…ሁለትን አነሳህ?
ናት፡   እየጠየኩህ እኮ ነው፡፡ ከዚያስ በኋላ ምን አለ?
ሞት፡ (በተከፈለ ልብ) ራስህ ታየዋለህ ምን አስቸኮለህ?
ናት፡   ስለዚህ የሚታይ ነገር አለ ማለት ነው?
ሞት፡ ምናልባት እንደዚያ ብዬ መግለፅ አልነበረብኝም፡፡ አሁን ጣል?
ናት፡ ውይ፤ አንተን ጠይቆ መልስ ማግኘት በጣም ከባድ ነው፡፡
ሞት፡   ካርታ እየተጫወትኩ እኮ ነው፡፡
ናት፡    እሺ፤ ያዝ፤ ተጫወት፡፡   
ሞት፡ ቀስ በቀስ ካርዶቼን በሙሉ ሰጥቼህ ልጨርስ ነው፡፡
ናት፡    የተጣሉትን ካርታዎች አትይ እንጂ!
ሞት፡ ኧረ አላየሁም፡፡ እያስተካከልኳቸው ነው። ማሸነፊያው ስንት ነበር?
ናት፡  አራት፡፡ ልትጨርሰው ነው?
ሞት፡ ማን ልጨርስ ነው አለ? የጠየቅሁት ማሸነፊያው ስንት እንደሆነ ብቻ ነው፡፡
ናት፡   እኔ ደግሞ የጠየኩህ በተስፋ ልጠብቀው የሚገባኝ ነገር መኖር አለመኖሩን ነው፡፡
ሞት፡  ተጫወት፡፡
ናት፡  በቃ አንዳንድ ነገር እንኳን አትነግረኝም? ቆይ ግን እኛ ወዴት ነው የምንሄደው?
ሞት፡ እኛ? እውነቱን ንገረኝ ካልክ አንተ እጥፍጥፍ ብለህ ወለሉ ላይ ነው የምትዘረረው፡፡
ናት፡  ኦ፣ እስኪደርስ በጣም ቸኮልኩኝ፡፡ ህመም ይኖረው ይሆን?
ሞት፡  ኧረ አፍታም አይቆይ፡፡
ናት፡   በጣም ደስ ይላል፡፡ (በእፎይታ ይተነፍሳል)
ሞት፡  በተሰቀለው፤ ስድስት የሳብክ መስሎኝ?
ናት፡ አይ፤ በል ሂድ፡፡ እና ወለሉ ላይ ነው የምሞተው ማለት ነው? ሶፋው ላይስ አልችልም?
ሞት፡  አይቻልም፡፡ ይልቅእየተጫወትክ….
ናት፡  ለምንድን ነው የማይቻለው?
ሞት፡  ምክንያቱም ወለሉ ላይ ነው የተፈቀደው! እስቲ አሁን ተወኝ፡፡ ጨዋታው ላይ ማተኮር እፈልጋለሁ፡፡
ናት፡   የግድ ወለሉ ላይ መሆን አለበት? ይሄንን ብቻ ነው የምጠይቅህ! ሶፋው ላይ ብሆን ምን ችግር አለው?
ሞት፡  ባክህ ቀጥል…
ናት፡ የጠየቅኩህ ይሄን ብቻ ነው፡፡ ሞ ሌፍኮዊትዝን (ኮሜዲያን) አስታወስከኝ፡፡ እሱም እንዳንተ ግትር ነበር፡፡ …ቅድም ግን በመጀመሪያ ሥራዬ ምናምን ስትል ምን ማለትህ ነበር?
ሞት፡   ምን ማለቴ ይመስልሃል?
ናት፡    ማንም ሰው ከዚህ በፊት ሄዶ አያውቅም ማለት ነው?
ሞት፡ ብዙ ሰው ሄዷል እንጂ፡፡ ግን እኔ አይደለሁም የወሰድኳቸው፡፡
ናት፡   እና ማን ነው?
ሞት፡  ሌሎች!
ናት፡   ሌሎችም አሉ እንዴ?
ሞት፡  ታዲያስ! እያንዳንዱ ሰው የሚሄድበት የራሱ የሆነ ሞት አለው፡፡
ናት፡   አላውቅም ነበር፡፡
ሞት፡ እንዴት ልታውቅ ትችላለህ? አንተ ማነህና ነው?
ናት፡   እንዴት ማነህ ትለኛለህ? እኔ…ምንም ነኝ እንዴ?
ሞት፡  ምንምማ አይደለህም፡፡ ቀሚስ አምራች ነህ፡፡ ስለ ዘላለማዊነት ምስጢራት ግን የት ታውቅና?
ናት፡   ምን እያልክ ነው? ጥሩ ገቢ አለኝ፡፡ ሁለት ልጆቼ ኮሌጅ በጥሰዋል፡፡ አንዱ ማስታወቂያ ሠራተኛ ነው፤ ሌላኛው ትዳር ይዟል፡፡ የራሴ ቤት አለኝ፡፡ ውሃ የመሰለች መኪና እነዳለሁ፡፡ ለሚስቴ የፈለገችውን ሁሉ አደርግላታለሁ፡፡ ደንገጡሮች፣ ውድ ልብሶች፣ ሽርሽር፡፡ አሁን ራሱ መዝናኛ ቦታ ነው ያለችው፡፡ በቀን ሃምሳ ዶላር ነው የሚከፈልበት፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት እኔም እሄዳለሁ…እና ምን ይመስልሃል…ማንም ተራ ሰው ነኝ?
ሞት፡   እሺ በቃ፡፡ ብዙ አይሰማህ!
ናት፡   ተሰማኝ አልኩህ?
ሞት፡  ቆይ እኔም ልክ እንዳንተ ቱግ ብል ምን ትላለህ?
ናት፡   እኔ ሰድቤሃለሁ እንዴ?
ሞት፡   እንዲህ ሆነህ ትመጣለህ ብዬ አልጠበኩም ነበር አላልከኝም?
ናት፡  ምን ጠብቀህ ነበር? ድግስ ደግሼ፣ በሆታና በእልልታ እንድቀበልህ?
ሞት፡ እንደዛ አይደለም፡፡ እኔን…አጭር ነህ፤ እንዲህ ነህ፤ እንዲያ ነህ…ያልከውን ማለቴ ነው፡፡
ናት፡  እኔን ትመስላለህ ነው ያልኩት፡፡ ራሴን በመስታወት እንደማየት እኮ ነው፡፡
ሞት፡ እሺ በቃ ይሁን፡፡
(ጨዋታቸውን ሲቀጥሉ ሙዚቃው እየጨመረና ብርሃኑ እየደበዘዘ መጥቶ ጨለማ ይሆናል፡፡ ቆይቶ መብራቱ ቀስ እያለ ይበራና ጨዋታው አልቆ ይታያሉ፡፡ ናት ውጤት ይቆጥራል፡፡)
ናት፡ ስድሳ ስምንት…ለአንድ መቶ ሃምሳ…በቃ፤ ተሸንፈሃል!
ሞት፡  (ካርታዎቹን በድብርት እየተመለከተ) ያቺን ዘጠኝ ቁጥር መጣል አልነበረብኝም፡፡ እናቷን!
ናት፡  በቃ ነገ እንገናኝ፡፡
ሞት፡ ነገ እንገናኝ ስትል ምን ማለትህ ነው?
ናት፡ አሸነፍኩህኮ …አንድ ተጨማሪ ቀን አገኘሁ ማለት ነው፡፡ አሁን ተነስተህ ሂድ፡፡
ሞት፡ የምርህን ነበር እንዴ?
ናት፡  ተስማምተን እኮ ነው የተጫወትነው?
ሞት፡ አዎ፤ ግን….
ናት፡ ግን… አትበለኝ ባክህ፡፡ ለሃያ አራት ሰዓት አሸንፌሃለሁ፡፡ ነገ ጠዋት ተመልሰህ ና!
ሞት፡  የምር ግን ለዚህ እየተጫወትን እንደነበር አላወቅሁም፡፡
ናት፡   በጣም ያሳዝናል፤ ልብ ብለህ ማዳመጥ ነበረብህ፡፡
ሞት፡  እና ለሃያ አራት ሰዓታት የት ልሄድ ነው?
ናት፡  የፈለግህበት! ዋናው ጉዳይ እኔ ተጨማሪ ሃያ አራት ሰዓት ማግኘቴ ነው፡፡
ሞት፡ መንገድ ለመንገድ ልንገላወድ ነው?
ናት፡  አልቤርጐ ተከራይ፤ ፊልም ወይም ሳውና ግባ…ነገሩን አታካብደው ባክህ!
ሞት፡ ውጤቱ ከእንደገና ይቆጠር፡፡
ናት፡  ደሞ ሃያ ስምንት ዶላር አለብህ፡፡
ሞት፡ ምን?
ናት፡  ሃያ ስምንት ዶላር! ይሄው የተፃፈውን …አንብበው፡፡
ሞት፡ (ኪሱን እየበረበረ) የተወሰነ ነገር አለኝ…ሃያ ስምንት ግን አይሞላም፡፡
ናት፡ ቼክም እቀበላለሁ፡፡
ሞት፡ ከየትኛው አካውንቴ?
ናት፡ ኧረ እዩልኝ… ከማን ጋር እንደምደራደር…?
ሞት፡ ብትፈልግ ክሰሰኝ፡፡ ቼክ የሚያስጽፍ አካውንት የት አለኝና?
ናት፡ እሺ፤ ያለህን ስጠኝ፤ ይበቃኛል፡፡
ሞት፡ ይሄንማ እፈልገዋለሁ፡፡
ናት፡  ምን ያደርግልሃል?
ሞት፡ ምንድን ነው የምታወራው፡፡ ወደማይቀርበት ልትሄድ አይደል እንዴ?
ናት፡ እና?
ሞት፡ ምን ያህል ሩቅ እንደሆነ አታውቅም?
ናት፡ እና ቢርቅስ?
ሞት፡ ለነዳጅ ከየት ላመጣልህ ነው? ድልድዩን ለመሻገር የሚከፈለው ገንዘብስ?
ናት፡  በመኪና ነው እንዴ የምንሄደው?
ሞት፡ እሱን ሲደርስ ታየዋለህ! ስማ ነገ ተመልሼ ስመጣ ይሄን ገንዘብ የማሸንፍበት ዕድል ትሰጠኛለህ። ካልሆነ ግን ትልቅ ችግር ውስጥ ነው የምገባው፡፡
ናት፡   የፈለግኸውን ያህል ጊዜ እንጫወታለን። ለቀጣዩ አንድ ሳምንት ወይም ወር ብንጫወትም ማሸነፌ አይቀርም፡፡ እንዳንተ አያያዝማ ለአመታት ጭምር አሸንፍሃለሁ፡፡
ሞት፡  አሁን ግን መድረሻ ቢስ ሆኜልሃለሁ፡፡
ናት፡  በቃ ነገ እንገናኝ፡፡
ሞት፡ (ወደ በሩ እያመራ) ጥሩ ሆቴል ያለው የት ነው? የምን ሆቴል ነው የማወራው?…ለካ ምንም ገንዘብ የለኝም፡፡ በቃ የሆነ ምግብ ቤት ውስጥ ቁጭ እላለሁ፡፡ (ጋዜጣውን አነሳ)
ናት፡  ውጣ! ውጣ! ጋዜጣዬን ደግሞ ቁጭ! (ጋዜጣውን ቀማው)    
ሞት፡ (እየወጣ ያጉተመትማል) መቼም ዝም ብዬ ልወስደው አልችልም ነበር፡፡ የግድ ካርታ መጫወት ነበረብኝ፡፡
ናት፡ (ጮክ ብሎ) ደረጃውን ስትወርድ ደግሞ ጠንቀቅ በል…ምንጣፉ እንዳያደናቅፍህ፡፡
(ከፍተኛ የመጋጨት ድምፅ ይሰማል፡፡ ናት በእፎይታ ይተነፍስና አልጋው አጠገብ ያለችውን ጠረጴዛ ተሻግሮ ስልክ ይደውላል፡፡)
ናት፡  ሄሎ፤ ሞ? እኔ ነኝ፡፡ ስማኝማ፤ የሆነ ሰው ሲፎግረኝ ይሁን ምን አላወቅሁም፤ ብቻ ሞት አሁን እዚህ ነበር፡፡ ከእኔ ጋር ትንሽ ካርታ ተጫወተ…አይደለም አይደለም፤ ሞት ነው ያልኩህ። ራሱ በአካል፡፡ ወይም ደግሞ ራሱን ሞት ነኝ ብሎ የሚጠራ ሰው፡፡ የሚገርመው ግን ሞ፤ እንዴት ያለ ደደብ መሠለህ!
(መጋረጃው ይወርዳል)

Published in ልብ-ወለድ

“ችሎታና ብቃት ካላቸው ወደ ትልልቅ ቴአትር ቤቶች ይገባሉ”

እድሜያቸው 18 ዓመት ሲሞላ ከህፃናትና ወጣቶች ቴአትር ቤት የሚሰናበቱ ወጣት አርቲስቶች የምንሰናበተው ያለ ሰርተፍኬትና ያለምስጋና በመሆኑ ቀጣይ እጣፈንታችን ያሳስበናል ሲሉ ስጋታቸውን ገለፁ፡፡ “በቅርቡ 50 ያህል በቴአትር ቤቱ ስናገለግል የቆየን ባለሙያዎች ልንሰናበት ቀናት ቀርተውናል” ይላሉ፡፡
የህፃናትና ወጣቶች ቴአትር ቤት ዳይሬክተር ወ/ሮ ፀጋነሽ አይናለም በበኩላቸው፤ “ህፃናቱ ችሎታና ብቃት ካላቸው ወደ ትልልቅ ቴአትር ቤቶች ይገባሉ፤ በድምፅ፣ በውዝዋዜና በመሰል ዘርፎች ማስታወቂያ ሲወጣ የድጋፍ ደብዳቤ እንፅፍላቸዋለን፤ የትም አይወድቁም” ብለዋል፡፡
“18 ዓመት ሲሞላን ከቴአትር ቤቱ እንደምንለቅ እናውቃለን” ያለው የዛሬ አራት ዓመት በ14 ዓመቱ ቴአትር ቤቱን የተቀላቀለ አንድ ወጣት፤ “ስንሰናበት ግን ቢያንስ ምስጋናና የምስክር ወረቀት እንኳን አለመሰጠቱ በቀጣይ ህይወታችን ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ ያሳድራል፤ ይህንን ከእኛ በፊት በተሰናበቱ ወጣቶች ላይ አይተነዋል” ሲል ስጋቱን ገልጿል፡፡
“ቴአትር ቤቱ 18 ዓመት ሞልቷቸው የሚሰናበቱ ወጣቶችን መድረሻ ማዘጋጀት አለበት” ያለው ሌላው ወጣት፤ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ በትያትር ቤቱ ውስጥ በድምፃዊነት ሲያገለግል እንደቆየ ጠቁሞ፤ ወጣቶቹ እንደ “ብሄር ብሄረሰቦች”፣ “አባይ”፣ “ላብ ደምን ይተካል”፣ “ምነው ሞት” የተሰኙ በአገር አቀፍ ደረጃ ታዋቂነትን ያተረፉ መዝሙሮችን በመዘመር፣ ህብረተሰቡን በማነቃቃት ረገድ ትልቅ ድርሻ ነበራቸው ብሏል፡፡ ሆኖም ሲሰናበቱ በየቲያትር ቤቶቹ እንዲመደቡ አልያም እንደ እድሜያቸው መጠን ሙያቸውን እንዲቀጥሉ የሚደረግበት መንገድ ባለማመቻቸቱ ወጣቶቹ ለስነ-ልቦናና ማህበራዊ ቀውስ መጋለጣቸው እንደማይቀር ከዚህ ቀደም ከተሰናበቱ ወጣት ባለሙያዎች ተሞክሮ አይተነዋል ብሏል፡፡
“ከዚህ ቀደም በጥረታቸው ትልልቅ ቦታ ከደረሱ ጥቂት የቴአትር ቤቱ ወጣቶች በስተቀር አብዛኛዎቹ የት እንደደረሱ አይታወቅም” ያለው ሌላው የ17 ዓመት ታዳጊ አርቲስት አንዳንዶቹ በተለያዩ ሱስ ውስጥ ወድቀው ሳንቲም ሲለምኑ የምናይበት አጋጣሚ አለ ይላል፡፡
“ስናገለግል የነበረው ለድምፃዊያን 40 ብር፣ ለተወዛዋዥ 20 ብር በወር እየተከፈለን ነው” ያለው ወጣቱ፤ ይህም ቢሆን አሁን ቀርቷል፣ አይከፈለንም ሲል አማሯል፡፡ “ባለን ብቃት፣ በምናሳየው እንቅስቃሴ ተወደን ቆይተናል፤ ይህን በማየት የአዲስ አበባ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ደሞዛችን 380 ብር እንዲሆን ከአንድ አመት በፊት ቢወስንም እስካሁን ተፈፃሚ አልሆነም” ብሏል - ወጣቱ፡፡
የቀድሞው የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ አቶ ኩማ ደመቅሳ፤ በብቃታቸው በመደነቅ ለእያንዳንዳቸው 10ሺህ ብር ሽልማት እንዳበረከቱላቸው የገለፁት ወጣቶቹ፤ ይህን በማግኘታችን ኃላፊዎች “እኛ እንሰራለን እናንተ ትጠቀማላችሁ” በማለት ሞራላችንን ጐድተውታል ብለዋል፡፡ “ቴአትር ቤቱ እስከዛሬ በብቃት ስናገለግል የቆየነውን ሙያተኞች ያለምስጋና፣ ያለ ምስክር ወረቀትና ከአመት በፊት የተወሰነልንን ደሞዝ ሳይከፍል፣ እንደሸንኮራ መጥጦ ሊጥለን ስለሆነ አፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጠን እንጠይቃለን” ሲሉ ተማፅነዋል፡፡
ለልማት ሲባል በትምህርት ቀን ሳይቀር እስከ አባይ ድረስ ሄደን በረሀ ሳይበግረን ስናገለግል ቆይተናል የሚሉት ወጣቶቹ፤ ከቴአትር ቤቱ ከወጣን በኋላ የምናርፍበት ቦታ አለመመቻቸቱ ያሳስበናል፤ የተከታዮቻችን ህፃናት ጉዳይም ያሰጋናል ይላሉ፡፡
የቴአትር ቤቱ ዳይሬክተር ወ/ሮ ፀጋነሽ ህፃናቱ ቀድሞውንም ቢሆን በቅጥር ሳይሆን ሙያ እንዲቀስሙ ተመልምለው የሚሰለጥኑ መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡
“እስካሁን ባለው ተሞክሮም ከህጻናትና ወጣቶች ቴአትር ቤት ወጥተው ትልልቅ ቦታ የደረሱ እንጂ ወድቀው ለመጥፎ ነገር የተጋለጡ አላውቅም” ያሉት ዳይሬክተሯ፤ ችሎታና ብቃት ካላቸው ወድቀው የሚቀበሩበት ምክንያት እንደሌለና የስራ ማስታወቂያ ሲወጣ የድጋፍ ደብዳቤ እንደሚፃፍላቸውም ተናግረዋል፡፡ ቴአትር ቤቱ እስከ ዛሬም ለትልልቅ ቴአትር ቤቶች ሲመግብ ቆይቷል፤ ቴአትር ቤቶችም ከህፃናትና ወጣቶች ወጥቶ ችሎታና ብቃት ካለው እንደማይጥሉ አብራርተዋል፡፡
በቅርቡ አዲስ መመሪያ እንደወጣ የተናገሩት የወ/ሮ ፀጋነሽ ከዚህ በኋላ ህጻናቱ እንዴት ይተዳደሩ፣ ስራቸው ከትምህርታቸው ጋር እንዴት ይጣጣም፣ ከቤተሰባቸው ጋር እንዴት ግንኙነት ይኑረን እና እንዴት እናንጻቸው” በሚለው ላይ እንደሚያተኩር ገልፀዋል፡፡ በቀጣይ ለሚሰናበቱትም ሰርተፍኬት ለመስጠት እንደታሰበ ተናግረዋል፡፡
ወጣቶች መዝሙር እንዲያቀርቡ በየመስሪያ ቤቶች ሲጠሩ ከ200-250 ብር በአንደ መድረክ እንደሚከፈላቸው የገለፁት ዳይሬክተሯ፤ የቀድሞው ከንቲባ አቶ ኩማ ደመቅሳ ሊሸልሟቸው ሲያስቡ አሁን ያሉትን ብቻ ሳይሆን በፊት እዚህ የነበሩትንም ፈልገው እንዲሸለሙ ማድረጋቸውን አስታውሰዋል።
የወጣው መመሪያ ለተተኪዎቹ ህፃናት መልካም አጋጣሚን እንደሚፈጥር የገለፁት ወ/ሮ ፀጋነሽ፤ አሁን ከሚሰናበቱት ወጣቶች ለተነሱት በርካታ ጥያቄዎች መልስ ለመስጠት በዳይሬክተርነት የተቀጠሩት በ2006 መስከረም ወር ላይ በመሆኑ እንደሚቸገሩ ገልፀዋል፡፡ “አሁን ስለሚሰናበቱት አብረዋቸው የነበሩትን መጠየቅ ትችላለችሁ፤ በቀጣይ አብሬያቸው ለምዘልቀው ግን በመመሪያው መሰረት በቁርጠኝነት ለመስራትና ህፃናቱን ትልቅ ደረጃ ለማድረስ ጥረት እያደረግሁ ነው” ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
ስማቸውን መጥቀስ ያልፈለጉ አንድ የወጣቶቹ የቅርብ ኃላፊ፤ የወጣቶቹ ችግር ወደ ቴአትር ቤቱ ሲመጡ ለተጨማሪ ሙያ ሳይሆን ህይወታቸው እዚህ ቴአትር ቤት እንደተመሰረተ አድርገው ማሰባቸው እንደሆነ ገልፀው፣ በጥረታቸው አንድ ነገር ላይ ለመድረስ መጣር እንጂ ብዙ ነገር ከቴአትር ቤቱ መጠበቅ እንደሌለባቸው ጠቁመዋል፡፡ ቴአትር ቤቱ የአቅም ውስንነት አለበት ያሉት እኚሁ ኃላፊ፤ ደሞዛቸው 380 ብር እንዲሆን ከዓመት በፊት መወሰኑን አምነው፤ ያልተከፈለበት የራሱ የሆነ ምክንያት እንዳለውና መግለፅ እንደማይፈልጉ ተናግረዋል፡፡   

Published in ጥበብ
Saturday, 31 May 2014 14:32

የጸሐፍት ጥግ

የአንዱ ደራሲና የሌላው ደራሲ ቃል አንድ አይደለም፡፡ አንዱ ሃሞቱን ቀዶ ሲያወጣ፣ ሌላው ከካፖርቱ ኪስ መዥርጦ ያወጣል፡፡
ቻርልስ ፔጉይ
በጣም ልታነበው የምትፈልገው መፅሃፍ ካለና ገና ያልተፃፈ ከሆነ፣ ራስህ ልትፅፈው ይገባል፡፡
ቶኒ ሞሪሰን
ከጥሩ ፀሐፊ የምወድለት የሚለውን ሳይሆን የሚያንሾካሹከውን ነው፡፡
ሎጋን ፒርሳል
ወረቀትህን በልብህ እስትንፋሶች ሙላው፡፡
ዊሊያም ዎርድስ ዎርዝ
የጨረቃዋን መፍካት አትንገረኝ፤ የብርሃኑን ፍንጣቂ በተሰበረ መስተዋት ላይ አሳየኝ፡፡
አንቶን ቼኾቭ
አንዳንዴ ቀለምና ወረቀት እፍ ፍያሉ ፍቅረኛሞች ይሆናሉ፡፡ ብዙ ጊዜ ግን ወንድምና እህት ናቸው። አልፎ አልፎ ደግሞ የለየላቸው ጠበኞች፡፡
ቴሪ ጉሌሜትስ
ተለዋጭ ዘይቤዎች (Metaphors) ግዙፉን እውነት በትንሽዬ ቦታ የመያዝ ብልሃት አላቸው።
ኦርሶን ስኮት ካርድ
የምፅፈው ታሪክ አዲስ አይደለም፤ ያለነው፤ በወጉ ተፅፎ የተቀመጠ፤ የሆነ ቦታ፤ አየሩ ላይ። ከእኔ የሚጠበቀው ፈልጐ መገልበጥ ብቻ ነው።
ጁሌስ ሬናርድ  

Published in የግጥም ጥግ
Saturday, 31 May 2014 14:31

የፍቅር ጥግ

ለእኔ ፍቅር ማለት አንድ ሰው “ቀሪውን ህይወቴን ካንቺ ጋር ለማሳለፍ እሻለሁ፤ከፈለግሽ ላንቺ ስል ከአውሮፕላን ላይ እዘልልሻለሁ” ሲለኝ ነው፡፡
ጄኒፈር ሎፔዝ
ጀግንነት ማለት ያለምንም ቅድመ-ሁኔታ ማፍቀር ነው፡፡ በምላሹ ምንም ሳይጠብቁ ማፍቀር፡፡ በቃ ፍቅር መስጠት፡፡ ይሄ ድፍረት ይጠይቃል፡፡ ራሳችንን ለጉዳት አጋልጠን መስጠት አንፈልግማ፡፡
ማዶና  
ፍቅር ሲይዝህ እንቅልፍ አይወስድህም፡፡ ምክንያቱም ተጨባጩ እውነታ ከህልምህ የተሻለ ነውና፡፡
ዶ/ር ሴዩስ
ከፍቅር የሚገኘው ደስታ ጊዜያዊ  ሲሆን  የፍቅር ስቃይ ግን  ለእድሜ ልክ ይዘልቃል፡፡
ቤቲ ዴቪስ
ልብ የሚፈልገውን ያውቃል፡፡ ለዚህ ምንም አመክኖ የለውም፡፡ አንድ ሰው ታገኛለህ፤ከዚያም ታፈቅራለህ፡፡ በቃ ይኼው ነው፡፡
ዉዲ አለን
ፍቅር ሲይዝህ ሁሉ ነገር እንደ ብርሃን ግልጥልጥ ይልልሃል፡፡
ጆን ሌኖን
በፍቅር ውስጥ ስትሆኚ  አደገኛ ስሜት መፈጠሩ አይቀርም---- የገዛ ልብሽን አሳልፈሽ ለሌላ ሰው እኮ ነው የምትሰጭው፡፡ ያውም በስሜትሽ ላይ የማዘዝ ስልጣን እንዳለው እያወቅሽ። ሁልጊዜም አይበገሬ ለመሆን ለምጥረው ለእኔ፣ ይሄ አደገኛ ነገር እንደሆነ አውቃለሁ፡፡  
ቢዮንሴ ኖውሌስ

Published in የግጥም ጥግ

ፋርዛና በአደባባይ ለ40 ደቂቃ በቤተሰቦቿ ስትደበደብ ፖሊስ በዝምታ አይቷል
ያለኔ ፈቃድ ባል በማግባት ስላዋረደችኝ ገደልና፤ አይፀፅተኝም - አባት
ፋርዛናን ለማግባት ብዬ ነው የመጀመሪያ ሚስቴን አንቄ የገደልኳት - ባል
የመጀመሪያ ሚስቱን ገድሎ ያልታሰረው ልጆቹ ይቅርታ ስላደረጉለት ነው - ፓሊስ

ባለፈው ማክሰኞ በፓኪስታን ላሆር ከተማ የተፈፀመው ዘግናኝ ግድያ ከቀን ወደ ቀን እየተወሳሰበ ነው፡፡ አጀማመሩ ግን እንዲህ ነው፡፡ “በፍቅር ግንኙነት ከአመት በላይ አሳልፈናል” በማለት የተናገሩት ፋርዛና ፓርቪን እና ኢቅባል መሐመድ፤ ተጋብተው አብረው ለመኖር ከወሰኑ ቆይተዋል፡፡ የፋርዛና ቤተሰብ ግን ፈቃደኛ አልሆነም፡፡
ፓርዛና የ25 ዓመት ወጣት ናት፡፡ ኢቀባል በእድሜ ይበልጣታል፤ ልጆችንም ወልዷል፡፡ ለፋርዛና ቤተሰብ ግን፤ ይሄ አላስጨነቃቸውም፡፡ ኢቅባል 1000 ዶላር ጥሎሽ አልከፍልም በማለቱ የተቆጡ የፋርዛና ቤተሰቦች፤ ለሌላ ባል ሊድሯት ተነጋግረው ጨርሰዋል፡፡ በዚህ መሃል ነው ባለፈው ጥር ወር ፋርዛና ያለ ቤተሰቧ ፈቃድ ከኢቅባል ጋር ተጋብታ የሄደችው፡፡ ቤተሰቦቿ ደግሞ ኢቅባልን ከሰሱት-“ልጃችንን ጠልፎ ወስዷል” በሚል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ እለት ፋርዛና ከኢቅባል ጋር ወደ ፍ/ቤት የመጣችው፣ “እኔ አልተጠለፍኩም” የሚል ምስክርነት ለመስጠት ነው፡፡ ኢቅባልን የከሰሱት ቤሰቦቿ… አባቷ፣ ወንድሞቿ፣ የአክስትና የአጐት ልጆች ሁሉ ተሰብስበዋል፡፡ ሃያ ይሆናሉ፡፡ ከፍርድ ቤት ስትወጣ ጠብቀው፤ ጠልፈው ሊወስዷት ቢሞክሩም እሺ አላለችም፡፡ ያኔ ነው ዙሪያዋን በመክበብ የድንጋይ መዓት ያወረዱባት - በአባቷ መሪነት፡፡
ባለቤቷ ኢቅባል እንደሚለው፤ ከፍ/ቤቱ በራፍ ላይ አደባባይ መሃል በጠራራ ፀሐይ በድንጋይ ሲወግሯት አላፊ አግዳሚ ሁሉ ከሩቅ ሆኖ ከመመልከት በስተቀር ለመገላገል የሞከረ ሰው የለም፡፡ ፖሊሶችም ነበሩ፡፡ የሦስት ወር እርጉዝ የነበረችው ፋርዛና ቶሎ አልሞተችም፡፡ ለ40 ደቂቃ በቤተሰቦቿ የድንጋይ ውርጅብኝ እንደተደበደበች የገለፀው ቢቢሲ፤ ይህንን የግድያ ጥቃት ለማስቆም ፖሊስ እንዳልሞከረ ዘግቧል፡፡ ፋርዛና በአሰቃቂ ስቃይ ህይወቷ ካለፈ በኋላ የታሰሩት አባቷ፤ ያለፈቃዳችን በማግባቷ አዋርዳናለች፤ ለክብራችን ስንል ገድለናታል፤ የሚፀፅተኝ ነገር የለም ብለዋል፡፡ በግድያው የተሳተፉ ወንድሞቿና ዘመዶቿ አልታሰሩም፡፡ ግን እነሱም በግድያው አልተፀፀቱም፡፡
እንዲያውም፤ ካሁን ቀደም ተመሳሳይ ግድያ እንደፈፀሙ ከመናገር ወደኋላ አላሉም፡፡ የዛሬ አራት አመት በተመሳሳይ የጋብቻ ውዝግብ ሰበብ ታላቅ እህቷን መግደላቸው በሲኤንኤን ተዘግቧል፡፡ ለነገሩ በፓኪስታን እንዲህ በቤተሰብ የሚፈፀም ግድያ አዲስ ነገር አይደለም፡፡ የፓኪስታን ምድር፤ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ተወካይ ዛህራ ዮሱፍ እንደሚሉት በየአመቱ አንድ ሺ ገደማ ሴቶች ያለ ቤተሰብ ፈቃድ አግብተዋል ተብለው ይገደላሉ፡፡
ዘግናኙ የግድያ ታሪክ በዚህ አልተቋጨም፡፡ የፋርዛና ባለቤት ኢቅባል ንፁሕ ሆኖ አታገኘም፡፡ ለካ፣ የዛሬ ስድስት አመት የመጀመሪያ ሚስቱን ገድሏል፡፡ ከፋርዛና ጋር ለመጋባት በማሰብ ነው የመጀመሪያ ሚስቴን አንቄ የገደልኳት ብሏል - ኢቅባል፡፡ አስገራሚው ነገር ከአንድ አመት በላይ አልታሰረም፡፡ ከመነሻውም በፖሊስ የታሰረው፤ “እናታችንን ገደላት” በማለት ልጆቹ በመመስከራቸው ነው፡፡ ከጥቂት ወራት በኋላ ደግሞ፤ ልጆቹ “ይቅርታ አድርገንለታል” ብለው ስለተናገሩ ከእስር መለቀቁን ሲኤንኤን ዘግቧል፡፡ የሴት ህይወት የረከሰባት ፓኪስታን፤ የቅዠት አገር አትመስልም?

Published in ከአለም ዙሪያ

ሃውኪንግ ለቀመሩ ክፍያ ተቀብሏል - ፓዲ ፓወር ከተሰኘው የቁማር ኩባንያ

      ከዩኒቨርስ አፈጣጠር እስከ አቶሞች ባሕርይ፣ በበርካታ የምልዐተ ዓለሙ ሚስጥራት ላይ የሚመራመር ታዋቂው የፊዚክስ ጥበበኛ ስቴፈን ሃውኪንግ፤ ሰሞኑን በእግር ኳስ ዙሪያ የምርምር ግኝቶቹን አቅርቧል።
በዘንድሮው የአለም ዋንጫ የእንግሊዝ ቡድን እንዴት ውጤታማ ሊሀን እንደሚችል ምክር የለገሰ ሲሆን፣ የ50 ዓመታት መረጃዎችን በመተንተን ለአሸናፊነት የሚያበቃ ቀመር (ፎርሙላ) አዘጋጅቷል። የተጫዋቾች አሰላለፍና የማሊያ ቀለም፣ የውድድር ሰዓትና የሙቀት መጠን፣ የፍፁም ቅጣት አመታትና የዳኞች ማንነት እንዲሁም ሌሎች በርካታ ተለዋዋጭ (variable) ነገሮችን ያካትታል - ቀመሩ።
በእርግጥ፤ የሃውኪንግ ቀመር ለሂሳብ ጠበብት እንጂ ለአብዛኛው ሰው ሊገባ የሚችል አይደለም። እንዲያውም፣ ነገሩን ይበልጥ ያወሳስብባቸዋል። ግን ችግር የለም። ስቴፈን ሃውኪንግ፣ ውስብስቡን ቀመር፣ በቀላል ቋንቋ ለማስረዳት ሞክሯል። ለምሳሌ፣ ለእንግሊዞች የሚስማማቸው መካከለኛ የሙቀት መጠን እንደሆነ ሳይንቲስቱ ጠቅሶ፤ የሙቀት መጠን በ5 ዲግሪ ሴንቲግሬድ ሲጨምር የቡድኑ ውጤታማነት በ59% ይቀንሳል ብሏል። በዚያ ላይ፣ እንደ አዲስ አበባ በመሳሰሉ ከፍታ ቦታ ላይ የእንግሊዝ ቡድን ማሸነፍ አይሆንለትም። የቦታው ከፍታ ከ500 ሜትር በታች ከሆነ ግን፤ የማሸነፍ እድሉ በእጥፍ ይጨምራል። ጨዋታው የሚጀመረው ከቀኑ ዘጠኝ ሰዓት ከሆነም፣ ቡድኑ ይቀናዋል።
ምን ዋጋ አለው? የሙቀት መጠን፣ የአካባቢው ከፍታና የውድድር ሰዓት፣ በምርጫ የሚወሰኑ ነገሮች አይደሉም። ነገር ግን የእንግሊዝ ቡድን የተጨዋቾቹን አሰላለፍና የማሊያውን ቀለም በትክክል ከመረጠ፣ የማሸነፍ እድሉን ማሻሻል እንደሚችል የሃውኪንግ ቀመር ያስረዳል። 4-4-2 አሰላለፍ ለእንግሊዝ እንደማይበጅ የገለፀው ሃውኪንግ፣ ቡድኑ ስኬታማ የሚሆነው በ4-3-3 አሰላለፍ እንደሆነና ቀይ ማሊያ መልበስ እንዳለበት ተናግሯል። ቀይ ማሊያ፤ በተቀናቃኝ ቡድን ላይ የስነልቦና ተፅእኖ ያሳድራል፤ እናም የእንግሊዝ ቡድን የአሸናፊነት እድሉን በ20% ያሻሽላል።
ሃውኪንግ እንደሚለው፤ ውድድሩ የሚካሄደው ቅርብ በሆነ አገር ቢሆን መልካም ነበር፤ ብራዚል ድረስ አትላንቲክ ውቅያኖስን ለማቋረጥ የሚደረገው በረራ፣ በተጫዋቾች ላይ ድካምን ይፈጥራል፤ የማሸነፍ እድላቸውንም በ22 በመቶ ይቀንሳል። ዳኞቹ አውሮፓውያን ሲሆኑ የእንግሊዝ ቡድን ይቀናዋል፤ አለበለዚያ ግን የማሸነፍ እድሉ በ25% ይወርዳል።
የቲፎዞና የአጃቢ ሴቶች ጉዳይስ? ይሄ በቡድኑ ውጤታማነት ላይ ምንም ለውጥ ስለማያመጣ በቀመሩ ውስጥ እንዳልተካተተ ሃውኪንግ ገልጿል።
ወደ ፍፁም ቅጣት የሚያመራ ውድድር ሲያጋጥምስ? የሃውኪንግ ምርምር፣ ሶስት ነባር ጉዳዮችን በድጋሚ ያረጋገጠ ሆኗል። አንደኛ፣ ፍጥነት ወሳኝ ነው። ፍፁም ቅጣት የሚመታ ተጫዋች፣ ቢያንስ ቢያንስ አራት እርምጃ መንደርደር አለበት።
ከዚህ ባነሰ እርምጃ ከተንደረደረ፣ ግብ የማስቆጠር እድሉ በግማሽ ይቀንሳል። ሁለተኛ፣ ከግራ ወይም ከቀኝ በኩል ከፍ አድርጎ መምታት ያስፈልጋል። 84 በመቶ ያህል ይሳካለታል። ኳሷን በደንብ ለመቆጣጠር በጎን እግር መምታት ነው። ሦስተኛ፣ ከተከላካይና ከመሃል ተጫዋቾች ይልቅ አጥቂዎች እንዲመቱ ማድረግ ያዋጣል ብሏል ሃውኪንግ።
ሳይንቲስቱ፣ ለእንግሊዞች ምክሩን ቢለግስም፣ ያሸንፋሉ የሚል ተስፋ የለውም። በቀመሩ መሰረት፣ ዋንጫውን የሚወስደው ብራዚል ነው። ግን የሳይንቲስቱ ምርምር ቀልጦ አይቀርም።
ከመነሻው፣ የፊዚክስ ባለሙያው ስቴፈን ሃውኪንግ፣ በእግር ኳስና በአለም ዋንጫ ላይ ጥናትና ምርምር ያካሄደው፣ ለእንግሊዝ ቡድን የማሸነፊያ ቀመር ለመፍጠር አይደለም። የሃውኪንግ ቀመር ለማንኛውም ቡድን ይሰራል። ያንን ቀመር የሚያሟላ ቡድን ያሸንፋል። ቀመሩን በእጅጉ ተፈላጊ የሚሆነው ግን፣ ሜዳ ውስጥ ገብተው በአለም ዋንጫው ለሚሳተፉ ቡድኖች አይደለም። ከዳር ሆነው ቁማር ለሚያጫውቱ ኩባንያዎች እንጂ። ስቴፈን ሃውኪንግም ቀመሩን ያዘጋጀው፣ ፓዲ ፓወር ለተሰኘ የቁማር ኩባንያ ነው - በክፍያ። እውነትም፣ የቁማር ኩባንያ ስኬታማ ሊሆን የሚችለው፣ በአንዳች የቀመር ስሌት የትኞቹ ቡድኖች ምን ያህል የማሸነፍ እድል እንዳላቸው የሚያውቅ ከሆነ ነው። አለበለዚያ ከፍተኛ ኪሳራ ሊደርስበት ይችላል። እናም፤ የሃውኪንግ ቀመር፣ የጊዜ ማሳለፊያ ጨዋታ አይደለም፤ የቢዝነስ መሳሪያ ነው።

Published in ከአለም ዙሪያ

እንግሊዝ ከቡድን ማጣሪያ እንደማታልፍ የገለፁት የጎልድማን ሳችስ ታዋቂ የባንክ ኤክስፐርተቶች፣ ብራዚል ብርቱ ተፎካካሪዎች ቢኖሩባትም ዋንጫ የማንሳት እድሏ ከፍተኛ ነው አሉ።
እልፍ አይነት መረጃዎችን በመተንተንና በማጠናቀር፣ ዙሪያ ገባውን አበጥሮና አንጥሮ፣ ፈጭቶና ጋግሮ፣ እጥር ምጥን ያለች ፎርሙላ መፍጠር፣ ለፊዚክስ ጠብተቶች ብቻ የተተወ ስራ አይደለም። በአለም ኢኮኖሚ ውስጥ ትልቅ ስፍራ የያዙ እንደ ጎልድማን ሳችስ የመሳሰሉ ባንኮች፤ የእለት ተእለት ስራቸው፣ መረጃዎችን ማበጠርና መፍጨት ነው። በቅርቡ፣ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ጤንነትን በሚመለከት፣ “ቢ” የተሰኘ ማርክ ሰጥተዋት መንግስት ምን ያህል እንደተደሰተ አላያችሁም? በመቶ የሚቆጠሩ አገራትን፣ በአስር ሺ የሚቆጠሩ ኩባንያዎችን እየፈተሹና እየመረመሩ፣ ማርክ ይሰጣሉ። በዚሁም መሰረት በቢሊዮን ዶላሮች ያበድራሉ፣ ኢንቨስት ያደርጋሉ፤ አክሲዮን ይገዛሉ፣ ይሸጣሉ። እንጀራቸው ነው። አሁን ደግሞ ለአለም ዋንጫ ተሳታፊ ቡድኖች ማርክ ሰጥተዋል።
ምን ይሳናቸዋል? ጨዋታዎችንና ጎሎችን፣ ድሎችንና ሽንፈቶችን፣ እንዲሁም ወቅታዊ ብቃትና ውጤቶችን በሚመለከት የ55 ዓመታት መረጃዎችን በመፈተሽ ነው የባንኩ ኤክስፐርቶች የራሳቸውን ቀመር ያዘጋጁት።
በባንኩ ቀመር መሰረትም፣ የዋንጫው ባለቤት ብራዚል ይሆናል። ለምሳሌ ከእንግሊዝ ቡድን ጋር ሲነፃፀር፣ የብራዚል የማሸነፍ እድል፣ ከ35 እጥፍ በላይ ይበልጣል። ምን ማለት መሰላችሁ? በውርርድ አንድ ብር ታስይዛላችሁ እንበል። ሁለት አማራጭ ይቀርብላችኋል። እንግሊዝ ያሸንፋል ብሎ የሚወራረድ፣ በአንዷ ብር 35 ብር ያገኛል። ብራዚል ያሸንፋል የሚል ካለ ደግሞ፣ በአንዷ ብር 2 ብር ያገኛል። ከእነዚህ ሁለት አማራጮች የትኛውን ትመርጣላችሁ? ከታዋቂው አለማቀፍ ባንክ ምክር የምትቀበሉ ከሆነ፣ “ብራዚል ያሸንፋል” ብላችሁ ለውርርድ ብታስይዙ ይሻላል።
ብራዚል በአለም ዋንጫው ወደ ሁለተኛ ዙር የማለፍ እድሏ ከ99 በመቶ በላይ ሲሆን፣ የእንግሊዝ እድል 54 በመቶ ያህል ነው። ለፍፃሜ የመድረስ እድላቸውስ? የብራዚል 60 በመቶ ሲሆን፣ የእንግሊዝ ግን ከ5 በመቶ ብዙም አይበልጥም።
ከብራዚል በመቀጠል ከፍተኛ ግምት የተሰጣት አርጀንቲና ነች። ከዚያ ደግሞ ጀርመንና ስፔን።

Published in ከአለም ዙሪያ

በብራዚል ከፍተኛ የታክስ ቅናሽ ተደርጎላቸው የተከፈቱ የነ ፓናሶኒክና የነ ሳምሰንግ ፋብሪካዎች፤ ዘንድሮ ከአምናው በእጥፍ የሚበልጥ ቴሌቪዥን አምርተው ለገበያ አቅርበዋል። በአንዲት ከተማ የተተከሉት ፋብሪካዎች፣ ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ 5 ሚሊዮን ቴሌቪዥኖች ፈብርከዋል። ለምን? ብራዚል ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኢኮኖሚ እድገቷ ቢደነቃቀፍም፤ ገዢ አይጠፋም... ብራዚላዊያን፤ ለአለም ዋንጫ የሚሆን ገንዘብ ከየትም ብለውያመጣሉ። በእርግጥም፤በየከተማው የሚገኙ ሱፐርማርኬቶችና የኤሌክትሮኒክስ እቃ መሸጫዎች፣ ባለፉት ሶስት ወራት ገበያ እንደደራላቸው ሲኤስ ሞኒተር ዘግቧል።
ባለ ሬስቶራንቶች፣ የግድ ተለቅ ያለ ቲቪ (ለምሳሌ የብራዚሉ ኮከብ ኔይማር የሚያስተዋውቀው የፓናሶኒክ ቲቪ) እንደገዙ ገልፀዋል - በ1500 ዶላር። ለመኖሪያ ቤት እየተሸጡ ያሉት ቲቪዎችም ዋጋቸው ቀላል አይደለም - አንድ ሺ ዶላር ገደማ ነው።

Published in ከአለም ዙሪያ
Saturday, 31 May 2014 14:27

የጎደለን ይኸው ነው!

ርዕስ - የሉሲ ከዋክብትና ሌሎችም (የልጆች መልካም ሥነ ምግባር መጽሐፍ)
የገፅ ብዛት - 145
የሽፋን ዋጋ - 30 ብር
የህትመት ዘመን - 2006 ዓ.ም
ደራስያን - ዊሊያም ጄ.ቤኔትና ሌሎች
ተርጓሚ - ገብረክርስቶስ ኃ/ሥላሴ
ቅድመ ኩሉ
የሃይማኖት ተቋማትና መምህራን የሚያስፈልጉት ከሞት በኋላ ስለሚኖረው ህይወት እንዲሰብኩን ብቻ ሳይሆን ምድራዊው ዓለም ጤናማና የተሳካ እንዲሆን ለማስቻል ጭምር መሆን አለበት ብዬ አምናለሁ፡፡ የሃይማኖት መሪዎች መኖርም መሞትም ያለባቸው በየእምነት መጻሕፍቱ የተደነገጉትን የመልካም ሥነ ምግባር ህግጋት በመጠበቅና በማስጠበቅ መሆን አለበት፡፡
የሃይማኖት አባቶች ጠንካሮች ከሆኑ ለመልካም ሥነ ምግባር ተገዥ በመሆን ምዕመናንን ከስህተትና ከበደል ከጠበቁ፣ ሀገር ሰላማዊና የፍቅር ምድር ትሆናለች፤ በአንጻሩ የሃይማኖት አባቶችና መሪዎች ከፍቅር፣ ከሰላምና መልካም ሥነ ምግባር ከራቁ፣ ምዕመናኑ ሰው መሆናቸውን ይረሱና የአውሬነት ምግባር ለማከናወን ይደፍራሉ፤ ፈጣሪያቸውን አይፈሩም፣ ፍቅርንና ሰላምን አያውቁም፤ የህይወታቸው ፍልስፍና ሁሉ የአሳማ ይሆናል - ዛሬን ብቻ ቀርበታን መሙላት፡፡
በዚህ መሃል የሀገር ፍቅር፣ የወገን ፍቅርና የቤተሰብ ክብር፣ ወዘተ ብሎ ቁምነገር አይኖርም። ይህ አይነት ድርጊትና እንዲህ አይነት ድፍረት ፈጻሚዎች ሲበዙ ሀገር ራቁቷን ትቆማለች፤ እናም ገመናዋ ሁሉ ሜዳ ላይ የተሰጣ ገብስ ይሆናል። ገመናዋ ከተጋለጠም የአላፊ አግዳሚው ሁሉ መዘባበቻ ትሆናለች፡፡
በሃገራችን ብዙ የልማት ተቋማት በመገንባት ላይ ናቸው፤ የትምህርት ተቋማት፣ የጤና፣ የውሃ፣ የመንገድ፣ የስልክ… ግን ያልተገነባ ትልቅ ቤት አለ - የህዝቡ አዕምሮ፡፡ በየቦታው የትምህርት ማዕከላት ቢገነቡም የትምህርት ጥራት የለም፤ ከክፍል ወደ ክፍል የሚታለፈው በመኮራረጅ መሆኑ በይፋ እየተነገረ ነው፡፡ አንዳንድ የግል ትምህርት ተቋማት እንዲያውም ጠንካራ ተቋማት ለመምሰል ኩረጃን ያበረታታሉ፡፡
“ይህንን ያህል ተማሪ አስፈተንን ይህን ያህሉ አራት ነጥብ እና ከዚያ በላይ አገኙ”  እያሉ ወላጅን ለማጭበርበር ይተጋሉ፤ ግን የትምህርቱ ጥራት የለም፤ በመሆኑም ዩኒቨርሲቲ ገብተው ስድስት ወር ሳይሆናቸው ተግበስብሰው ይባረራሉ፡፡ በኩረጀ ነዋ እዚያ የደረሱት፤ ጉዳዩ በዚህ ከቀጠለኮ አስኮራጅም ይጠፋና ከቻይና ወይም ከህንድ የኩረጃ አማካሪዎችን ለማስመጣት እንገደድ ይሆናል፡፡
እጅግ በርካታ ህንፃዎች በሚያስደንቅ ፍጥነት ይገነባሉ፡፡ ግን ከመመረቃቸው በፊት እንደ አክርማ መሰንጠቅ ይጀምራሉ፡፡ ይህ የትምህርት ጥራት መውደቅን የሚያመላክት ብቻ ሳይሆን የመልካም ሥነምግባር ህጸፅ ምልክትም ነው፡፡
ከተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች በሺህ የሚቆጠሩ የ”ህግ ባለሙያዎች” በየዓመቱ ይመረቃሉ፤ ግን በፍትህና መልካም አስተዳደር አካባቢ የሚሰማው እሮሮ ገና እልባት አላገኘም፤ ይህም የትምህርት ጥራት መውደቅ አንዱ ምልክት ነው ቢባል ስህተት አይመስለኝም፡፡
በርካታ የጤና ባለሙያዎች በየዓመቱ ይመረቃሉ፤ ግን አሁንም ብቁ ሙያተኞችን ማግኘት አዳጋች እየሆነ ነው፤ ብዙዎቹ የሙያ ብቃት ማነስ ብቻ ሳይሆን ከፍተኛ የስነምግባር ጉድለትም አለባቸው። በሰው የሚነግዱ ሞራለቡስ ሃኪሞች በከተማችን እየበዙ ናቸው፡፡ ይህ ጉድለት ከትምህርት ጥራት እና ከስነ ምግባር ጉድለት ጋር ላለመያያዙ ማስረጃ ማቅረብ የሚቸግር ይመስለኛል፡፡
የሃይማኖት ተቋማት እንደ ዓለማዊው ሁሉ በሙስና እየተድፈቀፈቁ ናቸው፤ በርካታ ባለሥልጣናት እንደ ውሻ እጅ እጅ የሚያዩ ናቸው። ይህ ሁሉ የትምህርቱ ሥርዓትና የሥነምግባር ትምህርት አለመኖር ያመጣብን ጣጣ ነው፡፡ መኮረጅ መስረቅ ነው፤ በኩረጃ ያደገ፣ ሰው ባለሥልጣን ሲሆን የሰው ኪስ መኮረጅ፣ የሃገርን ካዝና መኮረጅ ምን ሊያስደንቅ ይችላል?
አንድ ሰው የሚነቅዙና የማይነቅዙ የእጽዋት ዝርያዎችን ማወቅ ፈልጐ ጓደኛውን “ብሳና ይነቅዛል ጓዴ?” ብሎ ቢጠይቀው “ለእንጨቱ ሁሉ ማን አስተማረው!” አለው ይባላል፡፡ የሃይማኖት አባቶች፣ የትምህርት ቤት ኃላፊዎችና መምህራን ገና በለጋነታቸው ተማሪዎቻቸውን ኩረጃ የሚያስተምሩ ከሆነ፣ ከእነሱ የበለጡ እና እሳት የላሱ ሌቦችን እየመለመለሉ መሆናቸውን ማወቅ ይገባቸዋል፡፡ ለዛሬ ዳሰሳ የመረጥሁት መጽሐፍ ትኩረት ሊሰጥበት ስለሚገባ የህጻናት ጉዳይ የሚያወሳ ስለሆነ፣ ወቅቱም የ10ኛና 12ኛ ክፍል ፈተና የሚሰጥበት በመሆኑ የሚመለከታቸውን ሁሉ አደራ ማለት ተገቢ ነው ብዬ አምኜያለሁ፡፡

የመጽሐፉ ይዘት
መጽሐፉ በአራት ምዕራፎች ያተኩራል፤ 33 አጫጭር ታሪኮችና ግጥሞችን የያዘ ሲሆን ታሪኮችን የሚያጐሉ ልዩ ልዩ ስዕሎችም ተካትተውበታል። የይዘታቸው አበይት ቁምነገሮችም ሥራና ኃላፊነትን እንዴት መወጣት እንደሚገባ፣ ፍቅር፣ ርህራሄና ጀግንነት አስፈላጊ ጉዳዮች ስለመሆናቸው ሥነስርዓትና ቅንነት ለሰው ልጆች ስለሚያስገኙት ጥቅም፣ እንዲሁም እምነትና ትህትና ምን ያህል የከበረ ማህበራዊ ዋጋ እንዳላቸው የሚያስተምሩ ናቸው፡፡
ታሪኮቹ አጫጭርና ለህፃናት በሚመጥን መንገድ የተዘጋጁ ናቸው፡፡ አረፍተ ነገሮቹ አጫጭር ስለሆኑ ለንባብ ምቹ ናቸው፡፡ ከዚህም በላይ የተጻፉበት የፊደል መጠን ጉልህ በመሆኑ ህፃናት በቀላሉ ያነቧቸዋል፡፡
እነዚህ እና መሰል ታሪኮች በልጆች እንዲነበቡ ማድረግና ከተቻለም በሃገሪቱ ሥርዓተ ትምህርት ውስጥ ማካተት ጥቅሙ በዋጋ የሚተመን አይሆንም።

የሚጐድለን ይኸው ነው
ትምህርት ቤቶች በየአካባቢው ወይም በየቀበሌው ተሠርተዋል፤ ሆኖም ልጆች ስለመንደርተኛነት እንጂ ስለመልካም ሥነምግባር አይማሩም፤ ስለዘር ጥላቻ እንጂ ስለፍቅር አይዘምሩም፡፡ የሃገር ፍቅር ሳይሆን የገንዘብ ፍቅርን ተምረው ይወጣሉ፣ በኩረጃ ያድጋሉ፤ ሲኮርጁ ይኖራሉ፤ ማነንነታቸውንም አያውቁም”፡፡ የእነሱ ጀግና ከተፎ ሌባ እንጂ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፤ የሃገር ፍቅር የአላዋቂነት ወይም ያለመሰልጠን ምልክት ተደርጐ ይወሰዳል ምክንያቱም ህፃናት እንዲማሩ የተደረገው ይህንን ነዋ!
የሃይማኖት አባቶች ፍቅረ ሰብን ሳይሆን ፍቅረ ንዋይን ይሰብካሉ፤ መስበክ ብቻ አይደለም በገቢር ያሳያሉ፤ ምዕመኑ ፈጥኖ ይከተላቸዋል፡፡ ግን በሃይማኖቱ መጻሕፍት የተቀመጡት ህግጋት አፈር ድሜ በልተዋል፡፡ የዚህ ሁሉ ምክንያቱ የመልካም ሥነምግባር ትምህርት አለመኖር ነው፡፡
ወላጅ ለልጁ ልደት የሚያበረክተው ስጦታ የቻይና ሽጉጥ ወይም ቦምብ እንጂ መጽሐፍ አይደለም፤ ወላጆች እቤታቸው ቁጭ ሲሉ የካራቴ፣ የወንጀል፣ የወሲብና የጦርነት ፊልሞችን ያያሉ እንጂ መጽሐፍ ወይም ጋዜጣ በማንበብ ለልጆቻቸው አርአያ አይሆኑም የቋንቋ መምህራን ክፍል ውስጥ ይዘውት የሚገቡት ከተቀጠሩ ጀምሮ የሚያነበንቧትን ብቻ እንጂ መጻሕፍትን ወይም ጋዜጦችን በማምጣት ምርጥ ታሪኮችን በማንበብ፣ የተማሪዎቻቸውን የንባብ ፍቅር አያበረታቱም፡፡ በአንጻሩ በቦርሳቸው ውስጥ ጫትና ሲጋራ ሊይዙ ይችላሉ፡፡ ታዲያ ልጆች የት ያዩትንና ከማን የተማሩትን ቁምነገር ሥራ ላይ ያውሉ? ቀጣፊና ገፋፊ ባለሥልጣናት አገሪቱን ያጥለቀለቋት‘ኮ በዚህ ምክንያት ነው፡፡
በመጨረሻም መጽሐፉ በርካታ ቁምነገሮችን ያካተተ የመሆኑን ያህል፣ ስዕሎቹ ባለ ቀለም ቢሆኑ ኖሮ ተፈላጊነቱን ያጐላው ነበር ብዬ አምናለሁ። በተረፈ የትምህርት ሚኒስቴር፣ ወላጆችና አስተማሪዎች ለእንዲህ አይነቱ የመልካም ሥነምግባር ትምህርት ተገቢውን ትኩረት ብንሰጥ፤ ልጆቻችን አምላካቸውን ፈሪ፤ አገራቸውን፣ ወገናቸውንና ወላጆቻቸውን አፍቃሪ፣ ትሁታንና ቅኖች በመሆን እንዲያድጉ የላቀ ሚና መጫወት ይችላሉ የሚል እምነት አለኝ፡፡

Published in ጥበብ

          የ2014 ዳይመንድ ሊግ ትናንት በ3ኛዋ ከተማ በአሜሪካ ዩጂን፤ በፕሮፎንታይኔ ክላሲክስ ውድድር የቀጠለ ሲሆን ዛሬ የሚካሄዱት የወንዶች 800 ሜትር፤ 5ሺ እና 10ሺ ሜትር ውድድሮች ትኩረት ስበዋል። ዘንድሮ በአዲስ መልክ ከተጀመረ ለአምስተኛ ጊዜ የሚካሄደው ዳይመንድ ሊጉ በውድድሩ ዘመኑ ከፍተኛ ፉክክር የሚታይበት መሆኑን የተለያዩ መረጀዎች ገልፀዋል፡፡ የዳይመንድ ሊጉ የመክፈቻ ውድድር ከ2 ሳምንት በፊት በኳታር ዶሃ የነበረ ሲሆን በዚሁ ጊዜ በ800 ሜትር አሸንፎ ሙሉ ነጥብ ያስመዘገበው ኢትዮጵያዊው መሃመድ አማን ነበር፡፡ ከ2 ሳምንት በፊት ደግሞ ሁለተኛው ውድድር በቻይናዋ ከተማ ሻንጋይ ሲካሄድ የኔው አላምረው በ5ሺ ሜትር ድል በማድረግ መሪነቱን ይዟል፡፡
ፕሮፎንታይኔ ክላሲክስ  ትናንት  በሴቶች ረጅም ዝላይ፤  800 ሜትር፤ ዲስከስ ውርወራ እና በወንዶች አሎሎ ውርወራ የተጀመረ ሲሆን  በዛሬው እለት ከሚካሄዱ 14 ውድድሮች መካከል ደግሞ የወንዶች 10ሺ ሜትር፤ በሴቶች 3ሺ መሰናክል እና 1500 ሜትር፤ የወንዶች 5ሺ ሜትር እና 800 ሜትር ውድድሮች ይገኙበታል፡፡
በዘንድሮው የዳይመንድ ሊግ ውድድሮች በተለይ የ1500 ሜትር፣ የ800 ሜትር እንዲሁም የሌሎች የአጭር ርቀት ውድድሮች የዓለም ሪከርዶች የመስበር ዕድል አላቸው ተብሏል፡፡ ዛሬ በሚደረገው በወንዶች 800 ሜትር ለ1 ዓመት በጉዳት የቆየው ኬንያዊው ዴቪድ ሩዲሻ መሳተፉ ከባድ ትኩረት የተሰጠው ሲሆን በዚሁ ውድድር ከኢትዮጵያዊው መሃመድ አማን፤ ከቦትስዋናው ኒጄል  አሞስ ከእንግሊዙ አንድሪው ኦሳጄ እና ከአሜሪካው ድዋኔ ሶሎሞን ጋር በሚደረግ ፉክክር ሪከርድ ሊሰበር ይችላል ተብሏል፡፡ በኬንያዊው አትሌት ዴቪድ ሩዲሻ  ከ2 ዓመት በፊት በለንደን ኦሎምፒክ የተመዘገበው የ800 ሜትር የዓለም ሪኮርድ 1 ደቂቃ ከ41.54 ሰኮንዶች ነው፡፡የ20 ዓመቱ መሃመድ አማን እና የ25 አመቱ ዴቪድ ሩዲሻ ከ2010 ጀምሮ በ7 ውድድሮች ተገናኝተው አምስቱን ያሸነፈው ሩዲሻ ሲሆን ሁለት ጊዜ መሃመድ አማን ቀድሞታል፡፡
በሴቶች 1500 ሜትር የመጀመርያ ውድድሯን ሻንጋይ ላይ ያሸነፈችው የስዊድኗ አበባ አረጋዊ ለሁለተኛው ድል የምትሰልፍ ሲሆን አትሌት ገንዘቤዲባባ ስለሚኖራት ተሳትፎ ግልፅ መረጃ ባይገኝም ሌላዋ የ19 ዓመት ኢትዮጵያዊት አክሱማይት አምባዬ ትወዳደራለች፡፡ በ5000 ሜትር ወንዶች የመጀመርያ ውድድሩን ከሁለት ሳምንት በፊት በሻንጋይ ያሸነፈው ኢትዮጵያዊው የኔው አላምረው 24ኛ ዓመት ልደቱን በማክበር ሲሳተፍ ሌላው ኢትዮጵያዊ ሃጎስ ገብረህይወት ጨምሮ አሜሪካዊው በርናንድ ላጋት እና ሞ ፋራህ በክብር ተጋባዥነት ይፎካከራሉ፡፡
 ባለፉት 4 የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት ከ18 አገራት የተውጣጡ አትሌቶች በየውድድር መደባቸው የሊጉን ደረጃ ሰንጠረዥ በአንደኛነት በመጨረስ የዳይመንድ ዋንጫዎች እና የ43ሺ ዶላር ሽልማታቸውን ተቀብለዋል፡፡ በአጠቃላይ በ4 የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት 30 አሸናፊዎች በማስመዝገብ አንደኛ ደረጃ ያላት አሜሪካ ስትሆን፤ ኬንያ 21፤ ጃማይካ 10 እንዲሁም ኢትዮጵያ 7 ተሸላሚዎችን በማግኘት ተከታታይ ደረጃ አላቸው፡፡ በ5ሺ ሜትር ዳይመንድ ሊጉን ለሁለት ጊዜያት ያሸነፈው ኢማና መርጋ በ2010 እና በ2011 እኤአ ሲሆን በ2013 እኤአ ደግሞ የኔው አላምረው ተሸላሚ ነበር፡፡ በወንዶች 800 ሜትር ደግሞ አትሌት መሃመድ አማን  በ2012 እና በ2013 እኤአ ዳይመንድ ሊጉን አሸንፏል። በሴቶች 1500 ሜትር አበባ አረጋዊ በ2012 እኤአ በኢትዮጵያዊ ዜግነት እንዲሁም በ2013 እኤአ በስዊድናዊ ዜግነት የዳይመንድ ሊግ ተሸላሚ የነበረች ሲሆን መሰረት ደፋር በ5ሺ ሜትር  በ2013 እኤአ ያሸነፈች ሌላዋ ኢትዮጵያዊ አትሌት ናት፡፡

Page 2 of 21