ወ/ሮ ይድነቃቸው የሁለት ልጆች እናት ናት፡፡ ልጆቿ በመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀት ተኮትኩተው እንዲያድጉ ስለፈለገች፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ዕውቀትን በቀላል አቀራረብና ቋንቋ የያዙ የልጆች መፃሕፍት ፍለጋ ብዙ ቦታዎች ጠይቃ ማጣቷን ትናገራለች፡፡ የዚህች እናት ገጠመኝ በአገራችን ያለውን የመፃሕፍት ስርጭት ችግር ያመለክት እንደሆነ እንጂ ለሕፃናት የተዘጋጁ መፃሕፍት የሉም ወደሚል ድምዳሜ አያደርሰንም፡፡
የመፃህፍቱን ሥርጭት እንዲሁም ብዛትና ዓይነቱን ለማወቅ የሚቻልበት መንገድ የለም እንጂ ለሕፃናት የታለሙ በርካታ መፃሕፍት ተጽፈዋል፡፡ የደራሲ ማይክል ዳንኤል አምባቸው ሙት ዓመት በጣይቱ ሆቴል ሲከበር እንደተገለፀው፤ ሟቹ አብዛኛው በእንግሊዝኛ ቋንቋ ቢሆንም  40 የልጆች መፃሕፍትን አዘጋጅተው አሳትመዋል፡፡
በሌላ አጋጣሚ ደግሞ 49 የልጆች መፃሕፍት አሳትመዋል የተባሉ አንድ ደራሲ የማግኘት እድል ገጥሞኝ ነበር፡፡ የፃፏቸውን 49 የልጆች መፃሕፍት፣ በየክልሉ ባሉ ትምህርት ቤቶች ማከፋፈላቸውን ነግረውኛል፡፡
ለልጆች ታስበው የታተሙት መፃሕፍት ቁጥር ቀላል አይደለም፤ ይዘትና አቀራረባቸው ግን ብዙ ሊያነጋግር እንደሚችል እሙን ነው፡፡ በቅርቡ “የሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” በሚል ርዕስ በደራሲ ገብረክርስቶስ ኃይለሥላሴ የተዘጋጀው የልጆች መፅሃፍ፤ ልጆች መልካም ሥነ ምግባር እንዲማሩበት ታስቦ የተሰናዳ ሲሆን ለልጆች የሚዘጋጁ መፃሕፍት እንዴት መቅረብ እንዳለባቸው ጥሩ ማሳያ ይመስለኛል፡፡
በ145 ገፆች ተቀንብቦ የቀረበው መጽሐፉ፤ በአራት ምዕራፎች 36 ተረቶችን ይዟል፡፡ “ከአሁን ቀደም ከጓደኛዬ ጋር ‹ናብሊስ› በሚል ርዕስ ከ5ኛ እስከ 8ኛ ክፍል ላሉ ተማሪዎች ሊሆን የሚችል የልጆች መጽሐፍ አዘጋጅቻለሁ” ሲሉ በመግቢያው ላይ ያሰፈሩት ደራሲው “ይህ ጥረት በተመሳሳይ ሁኔታ መቀጠል እንዳለበት አጥብቄ ስላመንሁበት፣ ከ1ኛ እስከ 5ኛ ክፍል ለሚማሩ ተማሪዎች የሚሆን ተነባቢና ጣፋጭ ታሪኮችን በውርስ ትርጉም መልክ አዘጋጅቼ አቅርቤያለሁ” ብለዋል፡፡ ታሪኮቹ በ24 ስዕሎች ታጅበው ነው የቀረቡት፡፡
ደራሲ ገብረክርስቶስ፤ ለሕፃናት የሚዘጋጁ መፃሕፍትን በዕድሜና በክፍል ደረጃቸው እየለዩ ማቅረብ እንደሚገባ አስምረውበታል፡፡ ርዕሰ ጉዳዩ ምንም ይሁን ለአዋቂዎች እንዴት መቅረብ እንደሚችል፣ ለልጆችስ በምን መልኩ እንደሚዘጋጅ በደራሲው መፅሐፍ በተመሳሳይ ጭብጥ ከቀረብ ታሪክ ጋር ለማመልከት እሞክራለሁ፡፡
በ“ሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” መጽሐፍ ውስጥ ስለ ስስትና አልጠግብ ባይነት የቀረበው ታሪክ “ቀላዋጩ ሸረሪት” የሚል ርዕስ አለው፡፡ በድሮ ዘመን ሸረሪት ወገቡ ወፍራም ነበር፡፡ በአንዱ ዕለት ጫካ ውስጥ ያሉ ሁለት እንስሳት፣ በሁለት የተለያዩ መንደሮች ድግስ መሰናዳቱን ነገሩት፡፡ በሁለቱም ድግስ መብላት የፈለገው ሸረሪት፣ የትኛው ድግስ ቀድሞ እንደሚጀመር ስላላወቀ፣ ዘዴ ማፈላለግ ያዘ፡፡
“ወደ ቤቱ እየከነፈ ሄደና ረጃጅም ገመዶችን ያዘ፡፡ ሁለቱን ወንድና ሴት ልጆቹንም ጠራቸው፡፡ ልጆቹንና ገመዶቹን ይዞ ላይ ሰፈርንና ታች ሰፈርን በአማካይ ወደሚያዋስነው ወንዝ ሄዱ፡፡ አቶ ሸረሪት፤ በአንዱ የገመድ ጫፍ ወገቡን አሰረና ሌላኛውን ጫፍ ለሴት ልጁ ሰጣት፡፡ እርሷም የገመዱን ጫፍ እየጎተተች ወደ ታች ሰፈር ሄዳ፣ ግብዣው ሲጀመር ገመዱን በመሳብ ምልክት እንድትሰጠው ታዘዘች፡፡ በሁለተኛውም ገመድ በተመሳሳይ ወገቡን አስሮ፣ ጫፉን ለወንድ ልጁ ሰጠው፡፡ ወንድ ልጁም ወደ ላይኛው ሰፈር ሄዶ እንዲያመለክተው ታዘዘ፡፡ ሁለቱም ልጆቹ የታዘዙትን ለመፈፀም ወደየተመደቡበት ቦታ ገመድ እየጎተቱ ሄዱ፡፡ አቶ ሸረሪት ወገቡን በሁለት ገመዶች እንደታሰረ በመሀል ሆኖ ይጠባበቅ ጀመር…
“አጋጣሚ ሆኖ የሸረሪት ሀሳብ እንዳቀደው አልሆነም፡፡ የላይ ሰፈርና የታች ሰፈር የግብዣው ሰዓት ተመሳሳይ ሆነ፡፡ ሁለቱ የሸረሪት ልጆች፣ ግብዣዎቹ እንደተጀመሩ አባታቸው እንዳዘዛቸው ለመፈጸም ገመዶቻቸውን መሳብ ጀመሩ፡፡ ምስኪኑ አባት፤ ሸረሪት በሁለት አቅጣጫ በሚሳቡ ገመዶች ተወጥሮ በመሀል ተንጠለጠለ፡፡”
“ሸረሪት ወገቡ ቀጥኖ የሚታየው በዚህ ምክንያት ነው የሚለው ይህ ታሪክ በመቋጫ ላይ ልጆች አልጠግብ ባይና ስስታም እንዳይሆኑ የሚያስተምር ሀሳብ አቅርቧል፡፡
“በዓለም የታወቁ አጫጭር ልቦለዶች” በሚል ርዕስ በአምሳሉ አክሊሉ ተተርጉሞ፣ በ1981 ዓ.ም ለአንባብያን የቀረበው መጽሐፍም ስስትና አልጠግብ ባይነት ምን ጉዳት እንደሚያስከትል የሚያስተምር ታሪክ ይዟል፡፡ ከሩስያዊው ደራሲ ሊዎ ቶልስቶይ ሥራዎች ተወስዶ “ላንድ ሰው ምን ያህል መሬት ይበቃዋል?” በሚል ርዕስ በቀረበው ልቦለድ ውስጥ፣ አንድ ደሀና ምንም ያልነበረው ገበሬ፣ ሀብት ማካበትን ዓላማው አድርጎ መንቀሳቀስ ሲጀምር፣ የስግብግብና አልጠግብ ባይነት ስሜቱ አጉል አወዳደቅ ላይ እንደጣለው ያስቃኛል፡፡
የልቦለዱ ገፀ ባሕሪ ሚስት፣ ልጆች፣ ከሲታም ቢሆኑ የቤት እንስሳት፣ አነስተኛም ቢሆን የራሱ መሬትና ኑሮ ነበረው፡፡ ይህንን ኑሮውን ሌሎች ሲተቹበት ነበር ሀብት ለማፍራት መንቀሳቀስ የጀመረው፡፡ በምኞት፣ በጥረትና በድካም ከቦታ ቦታ እየተንቀሳቀሰ በርካታ መሬትና ሀብት አፈራ፡፡ ከእርካታ ጋር መገናኘት ግን ሳይቻለው ስለቀረ፣ የተጨማሪ መሬት ባለቤት ለመሆን ጉጉትና ፍላጎቱ እያየለ መጣ፡፡
በዚህ ወቅት ደግሞ ሊታመን በማይችል ዋጋ፣ የሰፊ መሬት ባለቤት ሊያደርገው የሚችል ዕድል አገኘ፡፡ አንድ ሺህ ሩብል ብቻ የሚከፍልበትን መሬት መርጦ፣ ለክቶና በቃኝ ብሎ የመወሰን መብት ነበረው፡፡ በዚህ መብት ውስጥ የተሰጠው ግዴታ ግን ነበር፡፡ የሚፈልገውን መሬት መርጦ ለመጨረስ፣ ፀሐይ ስትወጣ ጉዞ የጀመረበት መነሻ ላይ ጀምበር ስትጠልቅ መድረስ አለበት፡፡ የሚያየውን ለም መሬት ሁሉ ባለቤት ለመሆን ከመነሻው እየራቀ ስለሄደ፣ በመልስ ጉዞው ለብዙ ድካምና እንግልት ተዳረገ፡፡ ጀምበር ከመጥለቋ በፊት መነሻ ቦታ ላይ ቢደርስም ነፍስና ስጋው በምድር መኖር የሚያስችል አቅም አልነበራቸውም፡፡ አንድ ሜትር ጉድጓድ ተቆፍሮ እዚያው እንዲቀበር ሆነ፡፡
“ቀላዋጩ ሸረሪት” እና “ላንድ ሰው ምን ያህል መሬት ይበቃዋል?” የሚል ርዕስ ያላቸው ታሪኮች መሰረታዊ ጭብጥ አንድ ነው፡፡ ስስታምና አልጠግብ ባይነት በስተመጨረሻ ጉዳት ማስከተላቸው እንደማይቀር ትምህርት ይሰጣሉ፡፡
የሁለቱ ታሪኮች አቀራረብ ግን ተደራሻቸውን ታሳቢ ያደረጉ ናቸው፡፡ የደራሲ ገብረክርስቶስ ኃይለሥላሴ “የሉሲ ክዋክብትና ሌሎችም” መጽሐፍ፤ ለልጆች የሚዘጋጁ መፃሕፍት እንዴት መቅረብ እንዳለባቸው ማሳያ ሆኖ ሊቀርብ ይችላል ያልኩት በዚህ ምክንያት ነው፡፡

Published in ጥበብ

ባርሴሎና ለሊዮኔል ሜሲ ሰሞኑን በሰጠው አዲስ የኮንትራት ውል  ተጨዋቹን የዓለማችን ውዱ  ተከፋይ አድርጎታል፡፡ እስከ 2018 በኑካምፕ ለማቆየት በፈጸመው ስምምነት በየዓመቱ 16.3 ሚሊዮን ፓውንድ ይከፍለዋል፡፡ 20 ሚሊዮን ዩሮ ወይም 27 ሚሊዮን ዶላር ወይም 580 ሚሊዮን ብር  ማለት ነው፡፡ በዓለም ዋንጫ ሰሞን 27 ዓመቱን የሚደፍነው ሜሲ ባለፉት 11 ዓመታት ከባርሴሎና ጋር ለ8ኛ ጊዜ የኮንትራት ውል እና ማራዘሚያዎች መፈራረሙ ነው፡፡
የባርሴሎና የምንግዜም ከፍተኛ አግቢ ሲሆን በ425 ጨዋታዎች 354 ጎሎችን አግብቷል፡፡ 6 የላሊጋ፤ 3 የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ 2 የኮፓ ዴላሬይ እና ሌሎች በድምሩ 21 ዋንጫዎችን አግኝቷል፡፡
በአጠቃላይ ዓመታዊ ገቢ  እስከ 73 ሚሊዮን ዶላር የሚያገኘው  ክርስትያኖ ሮናልዶ ይበልጠዋል፡፡ የሜሲ 65 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡
 ለሊዮኔል ሜሲ እስከ 250 ሚሊዮን ፓውንድ የዝውውር ሂሳብ ይጠራል፡፡

በያቢ ፊልም ፕሮዳክሽን የተሰራው “ከቃል በላይ” የተሰኘ አስቂኝ የፍቅር ፊልም፣ የፊታችን ሰኞ በአቤል ሲኒማ ይመረቃል፡፡ በፊልሙ ላይ ወጣትና አንጋፋ ተዋንያን እንደተወኑበት የፊልሙ ፕሮዱዩሰሮች ገልፀዋል፡፡

በኢዮብ ጌታሁን የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተው “ያልተኖረ ልጅነት” መጽሐፍ በአሜሪካዊቷ ሻርሊን ቻምበርስ ቦልድዊን ወደ እንግሊዝኛ ተተረጎመ፡፡
“ኦርፋንስ ሶንግ” የሚል ርዕስ የተሰጠው ይኸው የእንግሊዝኛ ትርጉም፣ ከአማርኛው ጋር እንዳይጣረስ የመፅሐፉ ደራሲ በአርታኢነት ተሳትፎበታል፡፡ መፅሐፉ 270 ገፆች ያሉት ሲሆን በዋናነት ከኢትዮጵያ ውጪ እንዲሸጥ ታስቦ የተዘጋጀ ነው፡፡ የመፅሀፉም ዋጋ 14.95 ዶላር ነው፡፡ መጽሐፉ በኢትዮጵያ ውስጥ በቡክ ወርልድ የመፃህፍት መደብሮች ለሽያጭ ይቀርባል ተብሏል፡፡

በደራሲ መዓዛ ወርቁ “Desperate to Fight” በሚል በእንግሊዘኛ ቋንቋ ተፅፎ በሱንዳንስ ተቋም የምስራቅ አፍሪካ ሀገራት ውድድር ላይ የተመረጠው ተውኔት፤ “ከሰላምታ ጋር” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ ተተርጉሞ በኢትዮጵያ መታየት ሊጀምር ነው፡፡ ቲያትሩ ከዚህ ቀደም በእንግሊዝኛ ቋንቋ በኬንያ፣ በኒውዮርክ፣ በስቶክሆልም ስዊድን ለተመልካች ቀርቦ ተወዳጅነትን እንዳተረፈ ተገልጿል፡፡ በተጨማሪም በጀርመንኛ ቋንቋ ተተርጎሞ በጀርመን እና በአውሮፓ ለሚገኙ ተመልካቾች ለማቅረብ theatralize company ከደራሲዋ ጋር ኮንትራት ተፈራርሟል፡፡ ቲያትሩ የኬኒያ፣ የዩጋንዳ፣ የአሜሪካ እና የስዊድን ዜግነት ባላቸው ተዋንያን የተሰራ ሲሆን ለሀገራችን በሚቀርበው ተውኔት ላይ በቲያትር ሙያ የዳበረ ዕውቀት እና ልምድ ያላቸው አርቲስት ኤልሳቤጥ መላኩ እና ፈለቀ የማርውሃ አበበ እንደሚተውኑበት ታውቋል፡፡
በኪባ መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን ፕሮዱዩስ የተደረገው ይኸው ቲያትር፤ ከፊታችን ሰኞ ጀምሮ በጃዝ አምባ ላውንጅ በየሳምንቱ ለተመልካች ይቀርባል ተብሏል፡፡ ወደፊትም በሌሎች መድረኮች እንደሚቀርብ ለማወቅ ተችሏል፡፡   

በቀድሞው የኢትዮጵያ ንጉሰ ነገስት ቀዳማዊ ኃይለሥሴ ህይወት ዙሪያ የሚያጠነጥን

“RasTafari፡ The Majesty and the Movement` በሚል ርዕስ የተዘጋጀ ታሪካዊ ኤግዚብሽን ነገ በብሔራዊ ሙዚየም ይከፈታል፡፡
ኤግዚቢሽኑ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ በስልጣን ዘመናቸው ያበረከቷቸውን መልካም ተግባራት የሚዘክር ሲሆን፣ በፓን አፍሪካኒዝም ፅንሰ ሀሳብና በአፍሪካ የነፃነት እንቅስቃሴ ውስጥ ኢትዮጵያ የነበራትን ሁለንተናዊ አስተዋጽኦም ይዳስሳል ተብሏል፡፡ የአፍሪካ ጥቁር ህዝቦች፣ ቅኝ አገዛዝን ለመገርሰስ ስላደረጉት እልህ አስጨራሽ የነፃነት ትግልና አፍሪካውያን ወደ ትውልድ ምድራቸው ለመመለስ ያለፉባቸውን አስቸጋሪ ጉዞዎችም የሚቃኙበት እንደሚሆንም አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡
በኤግዚቢሽኑ ላይ ከሚቀርቡት የስዕል ሥራዎች መካከል በሰዓሊ ገ/ክርስቶስ ደስታ የተሰራው የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ምስልና በዕምአላፍ ህሩይ የተሳለው የእቴጌ መነን ምስል ተጠቃሽ ሲሆኑ  የአትላንቲክ የባርያ ንግድን የሚያሳዩ በርካታ ስዕሎች እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡
በፎቶግራፍ የኤግዚቢሽኑ ክፍልም ቀዳማዊ ኃይለሥላሴና እና የጋናው የቀድሞ ፕሬዚዳንት ክዋሜ ንክሩማን፤ የቀዳማዊ ሐይለስላሴ የጃማይካ ጉብኝት እንዲሁም የማርክስ ጋርቬይና የቦብ ማርሌይ ስራዎችን የሚያስታውሱ ምስሎች ይቀርባሉ፡፡  በ12 ምዕራፍ የተከፋፈለው ኤግዚቢሽኑ፤ ፊልሞችም የሚቀርቡበት ሲሆን የንጉሰ ነገስቱ ንብረት የነበሩ ቁሳቁሶችና ሌሎች ታሪካዊ ቅርሶች ለህዝብ ይታዩበታል ተብሏል፡፡
ኤግዚቢሽኑ ለአንድ ወር ክፍት ሆኖ የሚቆይ ሲሆን ከብሔራዊ ሙዚየም በተጨማሪ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የኢትዮጵያ ጥናት ተቋም የሚቀርብ ዝግጅት እንደሚኖረው ታውቋል፡፡ የፊታችን ረቡዕ ደግሞ ተመሳሳይ ኤግዚብሽን በሻሸመኔ በሚገኘው ሊሊ ኦፍ ዘ ቫሊ ሆቴል እንደሚከፈት ታውቋል፡፡ የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን ኤግዚቢሽን ያዘጋጁት የራስ ተፈሪያን ማህበረሰብ አባላት ሲሆኑ ላለፉት 4 ዓመታት በአሜሪካ፣ በእንግሊዝ፣ በጃማይካና በሜክሲኮ ከፍተኛ ዝግጅት ሲደረግ እንደቆየ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Published in ጥበብ

“የኢትዮጵያ ህያው ሙዚየም” የተሰኘ የሙዚየም ማውጫ ታትሞ ወጣ፡፡ በሀገሬ ሚዲያ ኮሙዩኒኬሽን የተዘጋጀው ይሄው የሙዚየም ማውጫ፤ በሁለት ከተማ አስተዳደሮችና በሌሎችም ክልሎች የሚገኙ ሙዚየሞችን ይዟል፡፡ 80 ገፆች ያሉት ማውጫው፤ በክፍል አንድ ከያዛቸው ሙዚየሞች ውስጥ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዚየም፣ የኢትዮጵያ ፖስታ ሙዚየም የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ተቋም ሙዚየም፤ በኦሮሚያ የሻሼ ሀውልትና ባህል ሙዚየም፣ በደቡብ ክልል የስልጤ ዞን ሙዚየም፣ የሆሌሎጂ ሙዚየም፣ የኮንሶ ሙዚየምና በተለያዩ ክልሎች ያሉ በርካታ ሙዚየሞችን አካትቷል፡፡ ሀገሬ ሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን ከዚህ ቀደም የቱሪዝም ማውጫዎችን ያሳተመ ሲሆን በቱሪዝም ላይ ትኩረት አድርጐ የሚሰራ ድርጅት ነው፡፡

አድናቂዎች ለዕጩዎቹ ድምጽ መስጠት ይችላሉ

ኢትዮጵያውያኑ ድምጻውያን አስቴር አወቀና ጃኪ ጎሲ፣ “አፍሪካን ሚዩዚክ ማጋዚን አዋርድስ” (አፍሪማ) ለተባለው ታላቅ አህጉራዊ የሙዚቃ ሽልማት በተለያዩ ዘርፎች በእጩነት ቀረቡ፡፡
አፍሪማ ሰሞኑን ይፋ ባደረገው የ2014 ሽልማት እጩዎች ዝርዝር ላይ እንደተጠቀሰው፣ ድምጻዊት አስቴር አወቀ በ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ሴት ድምጻዊት”፣ ጃኪ ጎሲ ደግሞ በ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ወንድ ድምጻዊ” ዘርፍ በእጩነት የቀረቡ ሲሆን፣ የሌሎች የአፍሪካ አገራት ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ቡድኖች፣ ማኔጀሮች፣ ዳይሬክተሮች፣ ፕሮዱዩሰሮች፣ ዲጄዎች፣ የዳንስ ቡድኖችና የሙዚቃ ቪዲዮዎችም በተለያዩ 26 ዘርፎች ለሽልማት ታጭተዋል፡፡
አስቴር አወቀ በታጨችበት የ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ሴት ድምጻዊት” ዘርፍ፣ ሌሎች ሁለት የኡጋንዳ፣ ሁለት የኬኒያና አንድ የታንዛኒያ ታዋቂ ድምጻውያን በእጩነት የቀረቡ ሲሆን፤ ጃኪ ጎሲ በቀረበበት የ“ምርጥ የምስራቅ አፍሪካ ወንድ ድምጻዊ” ዘርፍ ደግሞ፣ ሌሎች ሁለት የታንዛኒያ፣ ሁለት የኡጋንዳና አንድ የኬኒያ ድምጻውያን በእጩነት ቀርበዋል፡፡
አድናቂዎች http://afrimma.com/afrimma-nominees-2014/ በሚለው የድረ-ገጽ አድራሻ በመጠቀም ለሚፈልጓቸው እጩ ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ቡድኖችና ሌሎች እጩዎች ድምጻቸውን በመስጠት፣ አሸናፊ እንዲሆኑ የራሳቸውን ድጋፍ ማድረግ እንደሚችሉ የሽልማቱ አዘጋጆች ተናግረዋል።
በመጪው ሃምሌ ወር አጋማሽ በአሜሪካ ቴክሳስ ግዛት፣ ሪቻርድሰን ውስጥ በሚከናወነው የሽልማት ስነስርዓት ላይ፣ በአለማቀፍ ደረጃ እውቅናን ያተረፉ የተመረጡ አፍሪካውያን ድምጻውያን፣ ማኔጀሮች፣ ፕሮዲዩሰሮች፣ ዲጄዎች፣ ባህላዊ ተጽዕኖ ፈጣሪዎች በክብር ይሸለማሉ ተብሏል፡፡ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ከተለያዩ የአሜሪካ ግዛቶች የተጋበዙና ከ17 የአፍሪካ አገራት በክብር እንግድነት ተጋብዘው የሚመጡ ታላላቅ ጀግኖች ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የአፍሪካን ሙዚቃ የማስተዋወቅ አላማ ያለውና በየአመቱ በሚከናወን ደማቅ ስነስርኣት ለአሸናፊዎች የሚበረከተው ይህ ሽልማት፤ በዘርፉ ከሚሰጡ ታላላቅ አህጉራዊ ሽልማቶች አንዱ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በአለም አቀፍ ደረጃ ታዋቂ የሆኑ ድምጻውያንና የሙዚቃ ቡድኖች ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡበትና በቀጥታ የቴሌቪዥን ስርጭት ለእይታ የሚበቃውን የዘንድሮውን የአፍሪማ የሙዚቃ ሽልማት ስነስርዓት ስፖንሰር ያደረጉት የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ፓዎር ሃውስ ኢንተርናሽናል ኤርላይንና አክሴስ የተባለው የአሜሪካ ሶፍትዌር አምራች ኩባንያ መሆናቸውንም የሽልማት ድርጅቱ መስራች አንደርሰን ኦቢያጉ በድረ-ገጻቸው ላይ በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡

Published in ጥበብ
Saturday, 24 May 2014 15:04

የተከፈተው መስኮት

‹‹አክስቴ አሁን ትመጣለች›› አለች፤ ፍፁም ረጋ ያለችው የአስራ አምስት ዓመቷ ኮረዳ፡፡ ‹‹እስከዚያው ብቻዎትን እንዳይሆኑ ደግሞ ከእኔ ጋ ብንጨዋወት አይከፋም እ?››
እንግዳው፤ቅንነት ለተመላበት ንግግሯ አፀፋ የሚሆን ርዕሰ ጉዳይ ፈጥሮ እያወጉ ቢቆዩ፤ ወዲያውም አክስቷን በማስጠራት ከማስቸገር፤ በራሷ ጊዜ ተመልሳ እስክትመጣ ለመጠበቅም ጥሩ ይሆናል ሲል አሰበ፡፡ ወደዚህ የገጠር መንደር የመጣው፤ ስቃዩ እረፍት ለነሳው የነርቭ በሽታው መድኃኒት ፍለጋ ነበር፡፡ አሁን ግን፤ በዚህ ማንንም በማያውቅበት ስፍራ፤ የተመኘው እቅዱ መሳካቱን መጠራጠር ጀምሯል፡፡
‹‹ምን ሊፈጠር እንደሚችል አውቃለሁ!›› ብላው ነበር እህቱ፤ ወደ ገጠር ለመጓዝ አቅዶ ሲዘገጃጅ። ‹‹አንድም ሰው በማታውቅበት ሀገር፤ በባዳ ተከብበህ፤ የሚያናግርህ ፍጡር እንኳ አጥተህ፤ ይኼ ቁም ስቅልህን የሚሳይህ የነርቭ በሽታህ ባይተዋርነት ተጨምሮበት የባሰውን አንዘርዝሮ ነው የሚደፋህ!... ስለዚህ፤ እዚያ ስኖር ከምቀርባቸው ሰዎች ላንዳንዶቹም ቢሆን የአደራ ደብዳቤ ፅፌልህ እሱን ይዘህ ብትሄድ ነው የሚሻለው፡፡ አ…ዎ! መቸም እኔ እስከማውቃቸው፤ ድረስ በዚያ ከሚኖሩት ሰዎች መሀል ጥሩ ጥሩ ሰዎች አሉ፡፡››
እንግዳው፤ አሁን ቤቷ ውስጥ ቁጭ ብሎ የሚጠብቃትና እህቱ የአደራ ደብዳቤ ከፃፈችላቸው የመንደሩ ነዋሪዎች አንዷ የሆነችው ሴትም፤ ከነዚሁ ጥሩ ጥሩ ከተባሉት ሰዎች መካከል የምትመደብ ስለመሆኗ እርግጠኛ ሆኗል፡፡
‹‹በዚህ መንደር የሚኖሩ ብዙ ሰዎችን ያውቃሉ?›› አለችው የሴትዮዋ የእህት ልጅ፤ ለረዥም ሰዓት የነገሰውን ፀጥታ ለመስበር፡፡
‹‹ኧረ ማንንም! አንድ ብቻ!›› አለ እንግዳው ‹‹እርሷም እህቴ ናት፡፡› እህቴም ብትሆን አሁን ከተማ ነው የምትኖረው፡፡ ከአምስት አመት በፊት ግን እዚህ ነበረች፡፡ እናም አሁን ስመጣ፤ እዚህ ስትኖር በቅርበት ታውቃቸው ለነበሩ ሰዎች የአደራ ደብዳቤ ፅፋ…እሱን …አስይዛ…ነው የ.ላ.ከ.ች.ኝ፡፡››
የንግግሩ መጨረሻ አሳዛኝ ቅላፄ ነበረው፡፡
‹‹እንዲያ ከሆነማ ስለ አክስቴም ምንም ነገር አያውቁም ማለት‘ኮ ነው እ?›› አለች ረጋ ያለችዋ ጉብል፡፡
‹‹ከስምና አድራሻዋ በቀር አዎ›› አረጋገጠላት እንግዳው፡፡ አክስትየው ባለትዳር ሴት ልትሆን እንደምትችል ገመተ፡፡ ምናልባትም ባሏ የሞተባት ሴት፡፡ ግን ደሞ ላይሆንም ይችላል፤ በቤቱ ውስጥ የአባወራ አልባሳት ይታያሉ፡፡
‹‹አክስቴ፤ መከራ የመጣባት የዛሬ ሦስት ዓመት ገደማ ነበር፡፡ የእርስዎ እህት ከዚህ ወደ ከተማ ከሄዱ ከሁለት አመት በኋላ ማለት ነው፡፡››
‹‹የምን መከራ በሞትኩት?!›› አለ እንግዳው፡፡ በዚህ ሰላማዊ የገጠር ቀዬ፤ መከራ ምን ቢከብድ፤ በእኛ በከተማ ሰዎች ላይ የሚፈራረቀውን ያህል አይሆንም፤ ብሎ እየገመተ፡፡
‹‹መቼም እንዲህ ሥጋና አጥንትን በሚሰረስር የክረምት ቁር ይህን መስኮት ክፍቱን መተዋችንን ሲያዩ ሳይገረሙ አልቀረም፡፡›› አለችው የተረጋጋችዋ ትሁት፤ እጇን ዘርግታ፤ ልክ እንደ በር ተበርግዶ ክፍቱን የተተወውን፤ ከቤቱ ባሻገር ያለውን የለምለም ሳር ሜዳ በሩቁ የሚያሳየውን ሰፊ መስኮት እየጠቆመችው፡፡
‹‹አዎን…እሱስ ልክ ነሽ… ክረምቱ አውሎ ነፋስና ወጨፎ የቀላቀለ ዝናብ አለው፤ በጣምም ይበርዳል!›› አለ እንግዳው፡፡ ‹‹ግን ያልገባኝ ነገር፤ የመስኮቱ ክፍቱን መተው አክስትሽ ላይ ከደረሰው መከራ ጋር ምን እንደሚያገናኘው ነው?››
‹‹ልክ የዛሬ ሦስት አመት፤ የአክስቴ ባልና ሁለቱ ወንድሞቿ ለአደን ሲወጡ፡፡ ከዚህ መስኮት ስር ቆማ ነበር እርቀው ሲሄዱ በአይኗ የሸኘቻቸው፤ እናም አልተመለሱም፡፡ እንደወጡ ቀሩ፡፡ ለአደን ወደሚሰማሩበት ጥቅጥቅ ያለ ደን ለመድረስ የገጠሩን የድጥ መንገድ እያቋረጡ ሳለ፤ ሦስቱም ባንድ ላይ በአንድ ጥልቅ ማጥ ውስጥ ሰምጠው ቀሩ! ማጥ ዋጣቸው! አዩ እንግዲህ በዚያ ክረምት ብዙ ዘንቦ ነበርና፣ በሌሎች ክረምቶች ሲመላለሱ የኖሩባቸው ደረቅ ስፍራዎች ሁሉ ያለወትሯቸው በውኃና ደለል ተሞልተው፤ የላይኛው ሽፋናቸው ብቻ ርጥበቱ በነፋስ ተመጥጦ የደረቀ መስሎ ይታይ ነበር፡፡ ሬሳቸውም አልተገኘም፡፡ ከሁሉ የሚያሰቅቀውም ደግሞ ይኼ ነው፡፡›› ልጅቱ፤ ይኼን የሰቆቃ ታሪክ ስትተርክ፤ እስካሁን የነበራት መረጋጋትና የልጅነት ባህርይ ሁሉ ከፊቷ ላይ በንኖ ጠፍቶ፤ የአዋቂ ሰው ባህርይ ተላብሳ በፅኑ እየቆዘመች ነበር፡፡
‹‹ሌት ተቀን በሀዘን ተቆራምዳ የምትብከነከነው ምስኪኗ አክስቴ ታዲያ፤ ‹አንድ ቀን ከሄዱበት ተመልሰው ይመጡ ይሆናል› ብላ ተስፋ ታደርጋለች። ‹አንድ ቀን፤ እንደወትሯቸው፤ ግዳይ ጥለው ሲመጡ እንደሚደርጉት፤ ከማዶ ከጉብታው ማሳበሪያ ጀምረው እየፎከሩና እያቅራሩ፤ በኩራት እየተንጎማለሉ፤ ተከትሏቸው ሄዶ ከቀረው ዥንጉርጉር ውሻ ጋር መንደሩን አቋርጠው ወደ ቤት ሲቃረቡ፤ እኛም ስናደርገው እንደኖርነው፤ ተሯሩጠን መጥተን፤ በዚሁ መስኮት አሻግረን እናያቸዋለን› ትላለች፡፡ እናም ይኼ መስኮት፤ በየቀኑ ሳይዘጋ፤ ከንጋት አንስቶ እርጭ ያለ አስፈሪ ጭለማ እስከሚነግስበት እኩለ ሌሊት ድረስ እንዲሁ አፉ እንደተንቦረቀቀ የሚቆየው በዚህ የተነሳ ነው፡፡የፈረደባት አክስቴ፤ እየደጋገመች፤ ባሏ ነጭ የጥጥ ካፖርቱን እንዴት ክንዱ ላይ ጣል እንዳደረገ፤እንደ አይኗ ብሌን የምትሳሳለት ትንሽዬው ወንድሟ፤ ዘወትር ‹ተው! የነርቭ በሽታዬን ትቀሰቅስብኛለህ!› እያለች ስትቆጣው፤ ሆን ብሎ እሷን ለማናደድ የሚዘፍነውን ዘፈን እንዴት ጮክ ብሎ ያንጎራጉር እንደነበር፤ በቃ፤ ወደ አደን ሲወጡ የነበራቸውን አኳኋን አንድም ሳታስቀር እየዘረዘረች ሳትሰለች ታወራልኛለች፡፡ እና ታዲያ አሁን አሁን በእኔም ላይ ምን እየተፈጠረብኝ እንዳለ ልንገርዎት? ልክ እንዲህ ፀጥ ባለ አመሻሽ ላይ ብቻዬን ስሆን፤ ‹እውነትም፤ ተመልሰው ሲመጡ፤ በዚህ ሰፊ ክፍት መስኮት በሩቁ አያቸው ይሆናል‘ኮ!› የሚል፤ ዝብርቅርቅ ያለ የማይጨበጥ ሀሳብ ይሰፍርብኝ ጀምሯል፡፡ እናልዎት…››
ልጅቱ፤ በድንገት ንግግሯን አቋርጣ መንቀጥቀጥ ያዘች፡፡ አክስቷ፤  በቤቱ የጓሮ በር በኩል እየተጣደፈች ገብታ፤ እስካሁን ስለመዘግየቷ ይቅርታ ጠይቃው ስታናግረው፤ በጭንቀት የተለጎመው እንግዳ ውጥረቱ ረገብ አለለት፡፡
‹‹የኔ ነገር! ጠፋሁ አይደል፤ ቢጡ ስላለች ብቻህን አልቦዘንክም መቸም፤ አይደል?››
‹‹እ አዎን፤ በጣም ጨዋታ አዋቂ ልጅ ነች!›› አለ እንግዳው፡፡
‹‹ይኼ መስኮት ክፍቱን መሆኑስ አውኮህ ይሆን?›› አለች፤ ሴትዮዋ ፈገግ ብላ፡፡ ‹‹ባለቤቴና ሁለቱ ወንድሞቼ ለአደን ከሄዱበት ይመጣሉ፡፡ ዛሬ፤ ማዶ ማጡ አካባቢ ካለው ደን ጅግራና ቆቅ ሲያድኑ ነው የሚውሉ፡፡ እንግዲህ በጭቃ ተልኮስኩሰው መጥተው ምንጣፌን ሊያቆሽሹብኝ ነው ኤዲያ! እንዲያው ወንዶች ስትባሉ፤ እኛ ሴቶች ምን ያህል ለፍተን ቤት እንደምናፀዳ አይገባችሁምኮ! አይደል?››
ሴትየዋ፤ ስለ አደን ውሎ፤ በተለይ ቆቅና ጅግራን ማደን ስላለው አስቸጋሪ ውጣ ውረድ እየተፍነከነከች ያለማቋረጥ አወራች፡፡ ለእንግዳው ግን፤ የሚሰማው ነገር ሁሉ ፍርሀት የሚነዛ ጉዳይ ሆኖበታል፡፡ አቅሙ በፈቀደው መጠን፤ ርዕሰ ጉዳዩን ወደ ሌላ ሰላማዊ ወግ ለማስቀየር ቢሞክርም እንዳሰበው አልተሳካለትም። አንድ በደንብ የተረዳው ነገር ቢኖር፤ ይህቺ በአደራ ደብዳቤ የተቀበለችው ሴትዮ፤ ለእሱ ትኩረት ሰጥታ በእንግድነት ከማስተናገድ ይልቅ፤ ቀልቧ የተጠመደው፤ አስር ጊዜ ቀና እያለች በምታጨነቁርበት መስኮት ባሻገር በሚታየው ሰፊ የሳር ሜዳ ላይ መሆኑን ነው፡፡ በእርግጥም እንዲህ ባለ የሀዘን ድባብ ባጠላበት ስፍራ በእንግድነት መገኘቱ የዕድለቢስነት ስሜትን ያጭራል፡፡
‹‹ሀኪሞቹ፤ ተሰብስበው በተስማሙት መሰረት፤ የፃፉልኝ ትዕዛዝ፤ ሙሉ ለሙሉ እረፍት ማድረግ እንዳለብኝ የሚያስገድድ ነው፡፡ ማለትም፤ አንዳችም አይነት ጭንቀት፣ ሁከትና ግርግር ካለበት አካባቢ ገለል ብዬ፤ እንዲሁም ከማንኛውም አይነት ከበድ ያለ የሰውነት እንቅስቃሴን ከሚጠይቅ ተግባር ሁሉ ተቆጥቤ እንድቆይ ነው ያሳሰቡኝ፡፡›› አለ ሰውዬው፤ ማንኛውም እንደሱ ያለ እንግዳ ሰው፤ የበሽታው መንስኤ ታውቆለት መፍትሄ ያገኝ ዘንድ ማድረግ የሚጠበቅበትን፤ የህመሙን ደረጃ ተንትኖ ለማስረዳት፡፡ ‹‹አመጋገቤን በተመለከተ ግን፤ ሁሉም ሀኪሞች ገና በአንድ አይነት ውሳኔ ላይ አልደረሱም›› ሲል ቀጠለ፡፡
‹‹ገና?›› አለች ሴትዮዋ በተሰላቸ ድምፅ፡፡ ወዲያውም በፈገግታ ተሞልታና ቀልቧን ገዝታ ሙሉ ለሙሉ ወደ እሱ ዞረች፡፡ ግን እርሱ ለተናገረው ምላሽ ልትሰጠው አልነበረም፡፡
‹‹ይኸዋ መጡ!!›› ብላ ጮኸች፡፡ ‹‹ልክ በእራት ሰአት! እንዴት በጭቃ እንደቦኩ እዩዋቸው እስቲ በሞቴ?! መቃብር ፈንቅለው የወጡ አስከሬኖች አይመስሉም እናንተዬ?››
እንግዳው፤ በሽብር እየተንዘፈዘፈ፤ የሚያየው ነገር ሁሉ የፈጠረበትን ጥልቅ ሀዘን እንድታውቅለት ለማሳየት ቀ….ስ ብሎ ወደ ትንሷ ጉብል ዞር አለ። ልጅቱ ግን፤ በፍርሀት ተጎልጉለው የወጡ በሚመስሉት አይኖቿ፤ በተከፈተው መስኮት አሻግራ እያየች ነበር፡፡ እንግዳው፤ በተቀመጠበት ብርክ እየናጠው፤ ተንጠራርቶ፤ ሴትዮዪቱና ልጅቷ ወደሚያዩበት አቅጣጫ እሱም አብሯቸው አፈጠጠ።
ከቀድሞው በባሰ ሁኔታ በጠቆረው ድቅድቅ ጨለማ ውስጥ ሦስት፤ የሚንቀሳቀስ ጥላ መሳይ ገፅታዎች፤ ባሻገር የሚታየውን የለምለም ሳር ሜዳ እያቋረጡ፤ በቀጥታ ወደ ሰፊው መስኮት አቅጣጫ እየመጡ ነው፡፡ ሦስቱም፤ በየትከሻቸው ላይ ጠብመንጃ አንግተዋል፡፡ ከመካከላቸውም አንዱ፤ ነጭ የጥጥ ካፖርት ትከሻው ላይ ጣል አድርጓል። ለሀጩን የሚያዝረበርብ ዥንጉርጉር ውሻ፤ እያለከለከ እግር እግራቸው ስር ይከተላቸዋል፡፡ ሦስቱም በፀጥታ እስከ መኖሪያ ቤቱ ድረስ ከመጡ በኋላ፤ ልክ ወደ መስኮቱ ደፍ ሲጠጉ፤የጎረምሳው ጎርናና ድምፅ  የጨለማውን እርጭታ ጮክ ባለ ዘፈኑ ደበላለቀው፡፡
እንግዳው፤ አውልቆ በእጁ ይዞት የነበረውን ባርኔጣውን በሀይል ጨምድዶ ይዞ ድንገት ብድግ አለና እየተደነባበረ የቤቱን ዋና መግቢያ በር በርግዶ እግሬ አውጪኝ አለ፡፡ በአየር ላይ የበረረ እንጂ በእግሩ የሚሮጥ አይመስልም ነበር፡፡
‹‹ቤት እንደ ምን አመሻችሁ? እነሆኝ መጣንልሽ ውዴ!›› አለ ከሦስቱ በእድሜ ጠና ያለው፤ ነጭ የጥጥ ካፖርቱን ትከሻው ላይ ጣል እንዳደረገ፤ በመስኮቱ በኩል ብቅ ብሎ ከወገቡ በላይ እየታየ፡፡ ‹‹የረገጥነው ሁሉ ድጥ ብቻ ነበር፡፡ ገላጣ ገላጣው በነፋስ መድረቅ እየጀመረ ነው ብለን ስንረግጠው እያንሸራተተ ዱብ!... ማነው እሱ አሁን ከቤት ወጥቶ ሲሮጥ ያየነው ሰው?››
‹‹በጣም ግራ የሚያጋባ እንግዳ!›› አለች ሴትዮዋ ለባሏ፡፡ ‹‹ያደራ ደብዳቤ ይዞ ቤታችን ከደረሰ ጀምሮ የተናገረው አንድ ነገር ቢኖር፤ ያደረበት በሽታ እንዴት እንደሚያደርገው ብቻ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ልክ እናንተ ስትመጡ፤ ደህና እደሩም ሆነ ይቅርታ መሄዴ ነው ሳይል ድንገት ብርግግ ብሎ ሩጫውን አስነካው!ልክ እኮ ጣዕረ ሞት ያየ ነው የሚመስለው አሯሯጡ! ሆ!››
‹‹እኔ እንደሚመስለኝ ውሻውን ስላየ ነው›› አለች ረጋ ያለችዋ የሴትዮዋ የእህት ልጅ፡፡ ‹‹የውሻ ዘር የሚባል ሁሉ ክፉኛ እንደሚያስፈራው ሲነግረኝ ነበር። አንድ ምሽት ብቻውን ጭር ያለ የመቃብር ስፍራ ሲያቋርጥ፤ የውሾች መንጋ እጅብ ብለው ጥርሳቸውን እያፋጩ ሊነክሱት ኋላ ኋላው ሲከተሉት የሞት ሞቱን አመለጣቸው! ከእነሱ ለመሸሽ ሲሮጥ፤ ወዲህም ወዲያም እሚሸሸግበት ጥግ አጥቶ፤ ‹በቃ ዛሬ አለቀልኝ፤ ስጋዬን ቦጫጭቀው፣ አጥንቴን ቆረጣጥመው፣ ቅርጥፍጥፍ አድርገው አነከቱኝ!› ብሎ በሲቃ ሰቆቃ እያነባ፤ትረፍ ሲለው፤ፊት ለፊቱ አዲስ የተቆፈረ ትኩስ የቀብር ጉርጓድ አጋጠመውና ዘልሎ እዛ ውስጥ ገባ! ከዚያ በኋላ፤ እሱ ከታች ጠባቡ ጉርጓድ ውስጥ ሆኖ በስቃይ እየተወራጨ፤ ውሾቹ በጉርጓዱ አፍ ዙሪያ ከብበው ላዩ ላይ ሲጮኹና ላሀጫቸውን እያዝረበረቡ ሲያላዝኑበት መንጋት አይቀርም ነጋ! ነው ያለኝ፡፡ ታዲያ እንግዲህ አንድ ሰው ይህን አይነት መከራ ገጥሞት ለነርቭ በሽታ አይደለም ከዚያስ ለባሰ ልክፍት ቢጋለጥ ምን ይደንቃል?››
ቢጡ፤አንድን ታሪክ እሷ በፈለገችው መንገድ ቅልብጭ አድርጋ በማቅረብና በማስደመም በእጅጉ የተካነች ጉብል ናት - ፍፁም ረጋ ያለች ጨዋ፡፡

Published in ልብ-ወለድ

ውድ እግዚአብሔር-
ስለአንተ ሥራ አስተማሪያችን  ነግራናለች፡፡ አንተ እረፍት ስትወጣ ግን  ማነው የሚሰራልህ?
ዴቪድ-የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ፡፡ አንተስ?
ቤቢ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ትምህርት ቤት ስንማር፣ መብራት የፈጠረው ቶማስ ኤዲሰን ነው ተብለን  ነበር፡፡ ሰንበት ት/ቤት ደግሞ አንተ እንደፈጠርከው ነገሩን፡፡ ኤዲሰን ያንተን ሃሳብ ሰርቆብህ ነው አይደል ?
ዮኒ - የ7 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ህፃን ወንድም ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ እኔ ግን የጠየኩህ የምታምር ቡችላ እንድትሰጠኝ ነበር፡፡
ቤቲ- የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
ስለእኔ እንዳታስብ እሺ፡፡ ሁልጊዜ መንገድ ስሻገር ግራና ቀኙን በደንብ አይቼ ነው፡፡
ዳኒ-የ6 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
እሁድ እለት ቤተክርስትያን የምትመጣ ከሆነ አዲሱን ጫማዬን አሳይሃለሁ፡፡
ሚኪ-የ5 ዓመት ህፃን
ውድ እግዚአብሔር-
በዓይን የማትታየው ሰማይ ሩቅ ስለሆነ ነው አይደል?
ሳሚ- የ4 ዓመት ህፃን

Published in ጥበብ
Page 8 of 21