ሕብረት ባንክ ባለ32 ፎቅ የዋና መ/ቤት ህንፃ ለማስገንባት ከቻይናው ጂያንግሱ ኢንተርናሽናል ኩባንያ ጋር የግንባታ ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ከትናት በስቲያ በሂልተን ሆቴል በተደረገው የፊርማ ሥነ-ሥርዓት የህብረት ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ ታየ ዲበኩሉና በኢትዮጵያ የጂያንግሱ ሥራ አስኪያጅ ኢንጂነር ዙ ጃን የግንባታ የውሉን ኮንትራት ተፈራርመዋል፡፡ ባንኩ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በሊዝ በተረከበው 3,338 ካ.ሜ ቦታ ባለ 32 ፎቁ ህንፃ የሚገነባው በተለምዶ ሰንጋተራ በሚባለው አካባቢ ከንግድ ሥራ ኮሌጅ ፊት ለፊት እንደሆነ የጠቀሱት አቶ ታየ፣ ይህ እጅግ ዘመናዊ የዋና መ/ቤት ሕንፃ 119 ሜትር ቁመት (ከፍታ)፣ ምድር ቤቱ በአንድ ጊዜ 200 ያህል መኪኖች መያዝ የሚችል ባለ 4 ፎቅ መኪና ማቆሚያ የዋና መ/ቤት ቅርንጫፍ፣ የሰራተኞች መሰብሰቢያ አዳራሽ፣ የሥልጠና ክፍሎች፣ የሰራተኞች መዝናኛ በዓይነቱ ልዩ የሆነ የህንፃ መቆጣጠሪያ (ቢኤምኤስ) ስምንት ዘመናዊ አሳንሰሮች፣ የባንክ ሴኪዩሪቱ ሲስተምና ዳታ ማዕከል እንደሚኖረው ገልፀዋል፡፡
ለዋና መ/ቤቱ ህንፃ ዲዛይን በወጣው ጨረታ ከ40 በላይ አርክቴክቶች ተወዳድረው ሰባቱ ለመጨረሻው ዙር ሲያልፉ፣ ከፍተኛ የህንፃ ዲዛይን እውቀት ሙያ ባላቸው ዳኞች እስክንድር ውበቱና ሸሪኮቹ የአርኪቴክቸሮች አማካሪና ኢንጂነሮች ኩባንያ ጨረታውን ማሸነፉ ታውቋል፡፡
አሸናፊው ድርጅት የህንፃውን ዝርዝር ዲዛይን አዘጋጅቶ እየተቆጣጠረ የሾሪንግና የቁፋሮ ሥራው መጠናቀቁን የገለጹት አቶ ታየ ዲበኩሉ፤ የመሰረት ቁፋሮ በዚህ ወር ተጀምሮ ግንባታው በሶስት ዓመት ተኩል ያልቃል ብለዋል፡፡ (ጃንግሱ ኢንተርናሽናል ከቻይና ውጪ ባሉት ከ30 በላይ ቅርንጫፎቹ በርካታ ግንባታዎችን ያከናወነ ኮንትራክተር ነው፡፡ የወሰዳቸውን ፕሮጀክቶች የሚጨርሰው ከገባው ቀነ ቀጠሮ በፊት በመሆኑ፣ ይህንንም ፕሮጀክት በሦስት ዓመት ካልሆነም፣ በሦስት ዓመት ተኩል ይጨርሳል የሚል እምነት አለን” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

Published in ዜና

ባጋጠመው ህመም ምክንያት ለ14 ዓመታት በጀርባው ተኝቶ በርካታ የስዕል ሥራዎችን ሲሰራ የቆየውና በቅርቡ “ታላቅ የምስጋና የስዕል ኤግዚቢሽን” ያዘጋጀው ሰዓሊ ብሩክ የሺጥላና ሌሎች ታዋቂ የኪነጥበብ ባለሙያዎች ከህልፈታቸው በኋላ የዓይን ብሌናቸው ብርሃናቸውን ላጡ ወገኖች እንዲውል ለማድረግ በቃልኪዳን መዝገብ ላይ ሊፈርሙ ነው፡፡ ልገሳው ነገ ምኒልክ ሆስፒታል ቅጥር ግቢ ውስጥ በሚገኘው የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ ቢሮ ይካሄዳል፡፡
“እኔ ያየሁትን ሌሎች እንዲያዩ” በሚል በተዘጋጀው የልገሳ ዘመቻ፣ የልደት በዓሉን ምክንያት በማድረግ የዓይን ብሌኑን የሚለግሰውን የወጣቱን ሰዓሊ ብሩክ የሺጥላ አርአያነት ተከትለው ሌሎች ታዋቂ የኪነጥበብ ባለሙያዎች በልገሣ ቃል ኪዳን መዝገቡ ላይ እንደሚፈርሙ የኢትዮጵያ የዓይን ባንክ ምክትል ሥራ አስኪያጅ አቶ ደመቀ ከበደ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡ ከተቋቋመ አስራ አንድ ዓመት ያስቆጠረው የዓይን ባንኩ እስከ አሁን በብርሃን አሳላፊ መስታወት መጎዳት ምክንያት ዓይነስውር ለሆኑ 1170 ወገኖች ንቅለ ተከላ መከናወኑን የገለፁት ምክትል ሥራ አስኪያጁ፤ ካለው የታካሚ ቁጥር አንፃር ይህ እጅግ አነስተኛ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ ህክምናው የሚሰጠው ህብረተሰቡ በበጎ ፈቃደንነት ከህልፈት በኋላ በሚለግሰው የዓይን ብርሃን አሳላፊ መስታወቱ ሲሆን ይህን አካል የመለገሱ ባህል ከጊዜ ወደ ጊዜ መሻሻሎች ቢታዩበትም በቂ ሊባል የሚችል አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡ በቅርቡ የሰርግ ስነስርዓታቸውን ያከናወኑት አቶ ዮሴፍ ገብረስላሴና ወ/ሮ ፀሐይ ቦጋለ የተባሉ ሙሽሮች በቃልኪዳን መዝገቡ ላይ የፈረሙ ሲሆን ባንኩ ሙሽሮቹ ባሳዩት አርአያነት ያለው ተግባር ምክንያት የበጎ ፈቃድ አምባሳደር አድርጎ የሾማቸው መሆኑን አቶ ደመቀ ተናግረዋል፡፡
እስከ አሁን ከ10 ሺ በላይ በጎ ፈቃደኞች የዓይን ብሌናቸውን ከህልፈት በኋላ ለመለገስ ቃል ገብተው የፈረሙ ሲሆን ከእነዚህ በጎ ፈቃደኞች ውስጥ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ፤ አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴና አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን እንደሚገኙበት አቶ ደመቀ ገልጸዋል፡፡  

Published in ዜና

“ጮሃ የማታውቅ ወፍ እለቁ እለቁ ትላለች” - ሀገርኛ ተረት
አንዳንድ ታሪክ ሲውል ሲያድር እንደ ተረት ይወራል፡፡ ኢሮብ ትግራይ ውስጥ የምትገኝ አንዲት ወረዳ ናት፡፡ ተራራማ መልክዐ - ምድር ያላት ስትሆን ኢሮብ የሚባል ብሔረሰብ ይኖርባታል፡፡ የነደጃች ሱባጋዲስ (ማሸነፍን አበልፃጊ እንደማለት ነው) አገር ናት፡፡
በዚች አገር የሚታወቀው አንድ የነዋሪው ልማዳዊና ባህላዊ ጠባይ፣ መቻል፣ መታገሥና ሁሉን እኩል ማስተናገድ ነው፡፡ ህንፃም ልጅ ቢሆን፡፡ በሠርግ ወቅት የሚታደል ማንኛውም ነገር እንኳ ለልጅም እኩል ይደርሳል፡፡ ከተማይቱ ለጦርነት አመቺ ከሆኑት እንደ አሲምባ ተራራ እና አይጋ (ሻቢያ በጣም የተመታበት ቦታ) አሊቴና (ዳውሃን) ዓይነት ቦታዎች አካባቢ በመሆንዋ የደርግ ጦር፣ የኢዲዩ ጦር፣ የኢህአፓ ጦር፣ የህወሓት ጦር፣ አንዳንዴም የህዝባዊ ግንባር ጦር ወዘተ ኃይሎች እንደመተላለፊያ በየጊዜው እየመጡ ይሰፍሩባት ነበር ይባላል፡፡
ህዝቡ እነዚህን ኃይሎች በአግባቡ፣ ሳያጋጭና ሳያጣላ፤ አንዱን በፊት ለፊት አንዱን በጀርባ/ በጓሮ አስተናግዶ ኮሽ ሳይልበት ይሸኛቸዋል፡፡ ለኢሮብ ውይይት ዋና ባህል ነው፡፡ ህዝቡ የአገር ሽማግሌ ይኖረዋል፡፡ የእድር ዳኛ፣ የማህበር መሪ፣ የጎበዝ አለቃ ወዘተ እንደሚባለው ዓይነት የበሰሉ፣ ብልህነት የተዋጣላቸውና ህዝቡ እህ ብሎ የሚያዳምጣቸው አባት (አቦይ) ይኖሩታል፡፡
በአንድ ወቅት በዚሁ በኢሮብ አካባቢ ከፖለቲካ ንቅናቄ ድርጅቶች አንዱ ይመጣል፡፡ ህዝቡን ሰብስቦ እንደተለመደው ሰበካ ያደርጋል፡፡ ህዝብን ወክለው አቦይ ንግግር ያደርጋሉ፡፡ ጥያቄም ይጠይቃሉ፡፡
የንቅናቄ ቡድኑ አባላት በአቦይ ንቃትና አንደበተ ርቱዕነት ይደመማሉ፡፡ አቦይን በንቅናቄው ፖለቲካ ቢያጠምቋቸው የኢሮብ ህዝብ ላይ ትልቅ የፖለቲካ ተፅዕኖ ሊፈጥሩ እንደሚችሉ ገመቱ፡፡
ስለዚህም፤ አቦይን ለአሥራ አምስት ቀናት ወስደው የፖለቲካ ፕሮግራማቸውን ቢያስተዋውቋቸው ትልቅ ሥራ እንደሚሰሩላቸው ወሰኑ፡፡ አቦይን ይዘዋቸው ሄዱ፡፡ አቦይ ውይይቱን ተካፈሉ፡፡ ግምገማውን አዳመጡ፡፡ ትምህርቱን ቀመሱ፡፡
“አቦይ እየገባዎት ነው?” ይላል አንዱ ካድሬ፡፡
“አሳምሬ” ይላሉ አቦይ፡፡
ሌላው ሰበካውንና ገለፃውን ይጨርስና፣
“እህስ አቦይ! እየተከታተሉ ነው ትምህርቱን?”
“እንዴታ!” ይላሉ አቦይ፡፡
ሌላው ይቀጥላል፡፡
“አቦይ ዓላማችን ገባዎት?”
“አዎን”
“ፕሮግራማችን በዝርዝር ፍንትው ብሎ ታየዎት?”
“እጅግ! እጅግ!” ይላሉ፡፡
የአሥራ አምስቱ ቀን የአቦይ ንቃት ፕሮግራም አለቀ፡፡ ከዚያ አለቃው ካድሬ፤
“ይበሉ እንግዲህ አቦይ፣ ወደ ኢሮብ ጎሣ ይሂዱና እስካሁን የተማሩትን ያስተምሩ” አሉ፡፡
አቦይ አመስግነው ወደ ኢሮብ ተመለሱ፡፡
የኢሮብ ህዝብ ተሰብስቦ ጠበቃቸውና፤
“እሺ አቦይ ምን ተምረው መጡ?” አላቸው
አቦይም እንዲህ መለሱ፣
“ይገርማችኋል ወገኖቼ፣ የተማርኩት ስለዲሞክራሲ ነው፡፡ እናም በጣም ያስደሰተኝ ነገር በዲሞክራሲ ዝም ማለትም ይቻላል!” ብለው አጠቃለሉ፡፡
*       *      *
ብልህ ህዝብ ብልህ ዘመን ይሰራል፤ ይላሉ አበው፡፡ የተነሳበትን ቦታና ሁኔታ የማያውቅ ህዝብ የት እንድደደረሰ ለመገንዘብም ልብና ልቡና ያንሰዋል፡፡ የህዝብን ዐይን ይገልጣሉ፣ ያንቀሳቅሱታል የሚባሉ ማህበራት፣ ድርጅቶችና ፓርቲዎች፣ የነቁ፣ የተቡ፣ ሥነ - ምግባር የተላበሱና ከሁሉም በላይ አርቀው ማስተዋል የሚችሉ ሊሆኑ ይገባል። ታግለው የሚያታግሉ፣ ነቅተው የሚያነቁና የተደራጀ ህዝብ የሚከተላቸው መሆንም አለባቸው፡፡ ሥርዓትን መውለድ፣ ሥርዓታዊ አስተዳደርን ማበልፀግ አለባቸው፡፡ ገብረ ህይወት ባይከዳኝ ያሉትን እዚህ ላይ መጥቀስ አግባብነት አለው፡-
“አዕምሮ የሌለው ህዝብ ሥርዓት የለውም፡፡ ሥርዓት የሌለው ህዝብም የደለደለ ኃይል የለውም፡፡ የኃይል ምንጭ ሥርዓት ነው እንጂ የሠራዊት ብዛት አይደለም፡፡ ሥርዓት ከሌለው ሰፊ መንግስት ይልቅ ትንሽ ከተማ ሞያ ትሰራለች፡፡”
ሥርዓታዊ አስተዳደር ሲባል፣ ከሁሉም በላይ ገዢም ተገዢም የሚዳኙበትና የሚያከብሩት ደንብ ማለት ነው፡፡
ህዝብን የማያዳምጥ ፓርቲም ሆነ መንግስት ዕድሜ አይኖረውም፡፡ እኔ ያልኩት ብቻ ነው ትክክል ማለትም ብዙ መንገድ አያስኬድም፡፡
ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ እንዲህ ይሉናል፡- “እንደ ኢትዮጵያ ላሉ ደሀና ደካማ ሀገሮች ትልቁ አደጋ እንዲህ ያለ መንግስት ዘፈኔን ካልዘፈናችሁ፣ እስክስታዬን ካልወረዳችሁ እያለ ክብራቸውን ከመንካትም አልፎ ማለቅያ ወደ ሌለው ጦርነትና ውጥረት ውስጥ እንዳያስገባቸው ነው፡፡ በአሜሪካ ዳፋ ኢትዮጵያ ከዐረቦችና ሙስሊሞች ጋር ተጣላች ማለት፤ ከውጪም ከውስጥም በእሳት ስትለበለብ ኖረች ማለት ነውን፡፡ (ምን ዓለምን? የት ደረስን? ወዴትስ እያመራን ይሆን?)
ትውልዶች ያለሙት ዒላማ በየለውጡ ኩርባ (turning point) መመርመር አለበት፡፡ ምን ምን የሰመረ ነገር ታየ? ምን አጋጣሚ ተሳተ? ምን ምን ሥተት ተሰራ? ምን ላይ ፈር ቀደድን? ምን ላይ ባቡሩ ሐዲዱን ሳተ? ማለት ይገባል፡፡
የሄድንበት መንገድ አንዱ ችግር ቃልና አፈፃፀም አለመጣጣማቸው ነው፡፡ “በተለይ መብትን በተመለከተ፡፡ በሕገ - መንግሥት የተረጋገጡ መብቶች በተግባር ሲሻሩ ይታያሉ፡፡” ይላሉ ፀሐፍት በተደጋጋሚ፤ ስለ አፈፃፀም ችግር ሲያወጉ፡፡
ማንም ይፈፅመው ማን፤ ከየትኛውም ሀረግ ጋር ይጠላለፍ፤ ሙስናን መዋጋት ሌላው ግዴታችን ነው፡፡ እነ እገሌ ካሉበት ሙስናውን ማጋለጥ አደገኛ ነው እያሉ ገሸሽ ማለት ይሄው እዚህ አድርሶናል፡፡
“ኢትዮጵያ አንዴ በመደብ ስትመራ፣ አንዴ በብሔረሰብ ስትመራ ቆይታ፣ ወደፊት እጣ ፈንታዋ ከነዚህ ሁሉ የከፋው የሃይማኖት ጦርነት እንዳይሆን የብዙ ተመልካቾች ሥጋት ነው!” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ የሃይማኖትን አያያዝ ማወቅ ዋና ነገር መሆኑ ብቻ ሳይሆን ከጀርባው ያሉትንም ኃያላን ነቅቶ ማየት እጅግ ወሳኝ ነገር ነው፡፡ ጠንቀቅ እንበል፡፡
የሀገራችን ሌላው አስገራሚ ነገር ህዝብ ያደነቀውና ሆይ ሆይ ያለለት ታጋይ (ልክም ይሁን አይሁን) ሲገል ቆይቶ አንድ እክል ከገጠመው እንዳልነበር መረሳቱ ነው፡፡ ያላንተ ማናለን ሲባል የነበረ ታጋይ፣ መሪ ወይም ንቁ ሰው፤ ሲታሰር ወይም ካገር ሲወጣ ከአዕምሮአችን ጨርሶ ለመውጣት ሁለት ሳምንት አይፈጅበትም፤ ፈፅሞ ይረሳል፡፡ ያውም ምን አቅብጦት እዛ ነገር ውስጥ ገባ? ተብሎ ካልተተቸ ነው! ይሄ እንግዲህ ከዓመታት በፊት የተሰውለትን ሳይጨምር ነው!
ሌላው በእስከዛሬው መንገዳችን ያየነው ጉዳይ፣ የጠቅላይ ገዢነት አመለካከት ነው፡፡ በዝግ ባህላችን ላይ ይሄ ሲታከልበት “በደምባራ በቅሎ፣ ቃጭል ጨምሮ ነው!” ከዚህ ይሰውረን!
ፕሮፌሰር ባህሩ በዚያው ፅሑፋቸው፤ “ሁሉን አውቃለሁ ከማለት የሌሎችንም ሀሳብ ለማዳመጥ ዝግጁ መሆን፣ ሁሉንም ጠቅልዬ ልያዝ ከማለት ለመጋራት መዘጋጀት፣ ከሁሉም በላይ በስሙ የምንገዳደልበት ሰፊ ህዝብ የሚበጀውን አሳምሮ እንደሚያውቅ ተገንዝበን ከሱ መሬት የቆነጠጠ እውቀት ለመማር ዝግጁ መሆን ይኖርብናል፡፡” … በኢኮኖሚውም ረገድ፡፡ “የተማረ የሰው ኃይላችንን ተንከባክቦ መያዝ፣ ለግሉ ክፍለ ኢኮኖሚ ሰፊ ዕድል መስጠት የዕድገታችን መሰረት ነው… ከእርሻ ኢኮኖሚ ያገኘነው ቋሚ ድህነትንና ተደጋጋሚ ረሀብን ብቻ ነው፡፡ የትም ያላደረሰንን በጥቃቅን የገበሬ ማሳዎች ላይ የተመሰረተውን የእርሻ ኢኮኖሚ ትተን ወደ ኢንዱስትሪያል ኢኮኖሚ በፍጥነት የምንሸጋገርበትን ስልት ስናወጣ ነው የምናድገው” ይሉናል፡፡ የሰብዓዊ መብቶችም ሆኑ የዲሞክራሲ መብቶች በልካችን እንዲሰፉ የታሰበ እለት “መላው ቀለጠ!” “ገደደ!” ማለት ብቻ ነው የሚተርፈን፡፡ የመናገርና ሀሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት የምንታገልለት፣ ሳናሰልስ የምንጮህለት፣ መቼም ወደ ኋላ የማንልበት ጉዳይ ቢሆንም፣ የማይጥመን ነገር ካለ፣ የአቦይን በሳል አስተሳሰብም እንጋራለን “በዲሞክራሲ ዝም ማለትም ይቻላል!” እንላለን፡፡  

Published in ርዕሰ አንቀፅ

   ማሽኖችን በአልኮል መጥረግና በላይተር ማቃጠል በሽታ ከማስተላለፍ አያድናቸውም ከወራት በፊት በራስ ቅሉ መሀል ላይ የወጣችው ጭርት መሳይ ነገር መላ ጭንቅላቱንና አንገቱን ለማዳረስ የፈጀባት ጊዜ ጥቂት ሳምንታት ብቻ ነበር፡፡ ከራስ ቅሉ እየተቀረፈ በብናኝ መልክ በኮቱና ሸሚዙ ላይ በሚራገፈው ነገር መሳቀቁ ሲበዛበትና ችግሩ ሲበረታበት መፍትሄ ፍለጋ የቆዳ ሐኪሞች
ወዳሉበት አለርት ሆስፒታል ሄደ፡፡ ምርመራ ያደረገለት ሃኪምም በፈንገስና በባክቴሪያ ሳቢያ የሚከሰት “ኢንዳፎሊግላይት” የተባለ የቆዳ በሽታ እንደሆነ ነገረው፡፡ ተከታታይነት ያለው ህክምና
ማድረግ እንዳለበትና በሽታው ወደ ሌሎች ሰዎች እንዳይተላለፍ መጠንቀቅ እንደሚገባው አሳስበው፡፡ በሽታው በአብዛኛው በፀጉር ቤት ማሽኖችና ፎጣዎች ከሰው ወደ ሰው እንደሚተላለፍም ነገረው፡፡ ነገሩ ግን ለማስረሻ ፈፅሞ አልተዋጠለትም፡፡ ላለፉት አራት አመታት አንድ የፀጉር አስተካካይን በደንበኝነት ይዞ ነው የቆየው፡፡ ጸጉሩንም ሆነ ፂሙን ለመስተካከል ወደ ፀጉር ቤቱ በሄደ ጊዜ አስተካካዩ ማሽኑን በአልኮል አፅድቶና በላይተር አቃጥሎ ነው የሚያስተካክለው፡፡ ታዲያ ባክቴሪያው እንዴት ወደ እሱ ሊተላለፍ ይችላል? ሌላ መንገድ መኖር አለበት … ብሎ ነበር የገመተው፡፡ አሁን ለወራት ሲያሳቅቀው ከቆየው ችግር ለመላቀቅ የሚያስችለውን ህክምና በአለርት ሆስፒታል ጀምሮ ጥሩ መሻሻሎችን እያየ መሆኑን ገልፆልኛል፡፡ በዚህ ወጣት ላይ የደረሰው አይነት ችግር በበርካታ ኢትዮጵያውያን ወንዶች የፀጉር ቤት
ተጠቃሚዎች ላይ ሊደርስ ይችላል፡፡ የዚህን ወጣት ገጠመኝ መነሻ አድርገን በከተማችን የተለያዩ አካባቢዎች ወደሚገኙ የወንዶች ፀጉር ቤቶች ተዘዋውረን የሚጠቀሙባቸውን ማሽኖችና የንፅህና አጠባበቃቸውን ለማየት ሞክረናል፡፡ በመሳለሚያ፣ በመርካቶ፣ በፒያሳ፣ በሰሜን ሆቴል፣ አዲሱ ገበያ፣ ጦር ኃይሎችና ሜክሲኮ፣ ስድስት ኪሎና ሽሮሜዳ ተዘዋውረን የተመለከትናቸው አንዳንድ የወንዶች ጸጉር ቤቶች የማሽኖቻቸውን ንፅህና በስቴራላይዚንግ መሳሪያ እንደሚጠብቁ የሚገልፁ ታወቂያዎችን ቢለጥፉም የማፅጃ መሳሪያው ግን የላቸውም። አሊያም ደግሞ አገልግሎት
መስጠት አቁሟል። ደንበኞቻቸውን ለማጭበርበር ምንም አይነት አገልግሎት በማይሰጡ የስቴራላይዘር መሳሪያ ውስጥ የፀጉር መቁረጫ ማሽኖቹን ለደቂቃዎች ይከቱና ያወጧቸዋል፡፡ ንዳንዶቹ ደግሞ ማሽኑን በአልኮል ጠረግ ጠረግ ያደርጉና በላይተር እሳት ሞቅ ሞቅ ያደርጉታል፡፡
የጸጉር ማበጠሪያዎች፣ የፊትና የራስ ቅል የሚጠረግባቸው ቁርጥራጭ ፎጣዎችና በአንገት ዙሪያ የሚታሰሩት ጨርቆች ግን ንፅህናቸው በምን መልኩ እንደሚጠበቅና ምን ያህል ለጤና አስተማማኝ
እንደሆኑ ጠያቂም ምላሽ ሰጪም የለም፡፡
ጸጉር አስተካካዩ ሥራውን ካጠናቀቀ በኋላ በረዳቱ በሚቀርብለት ውሃ ውስጥ እየነከረ የደንበኛውን
የራስ ቅልና ፊት የሚያፀዳበት ቁራጭ ፎጣን ንፅህና ጠይቀን የምናውቅ ስንቶቻችን እንሆን? የፀጉር ማስተካከያ ማሽኑ ንፅህና የሚያሳስበንን ያህል ስለ እነዚህ ቁርጥራጭ ፎጣዎችና ስለ ማበጠሪያዎቹ አስበንና ተጨንቀንስ እናውቅ ይሆን? ባልታከሙ የፀጉር ቤት ማሽኖችና መሳሪያዎች አማካኝነት የሚከሰቱ የጤና ችግሮች አሳሳቢ ሲሆኑ
ዩኒቨርሲቲ ህክምና ፋክሊቲ የጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የቆዳና አባላዘር በሽታዎች ስፔሻሊስት ዶክተር
አብርሃም ተመስገን ይህንን ጉዳይ አስመልክተው ሲናገሩ፤ “የፀጉር ቤት ማሽኖች ለዚህ በተዘጋጀ የማፅጃ መሳሪያና በፈሳሽ ኬሚካል ማፅጃዎች ካልፀዱና በበቂ የሙቀት ኃይል እንዲቃጠሉ ካልተደረገ በስተቀር ኤችአይቪ/ ኤድስን ጨምሮ ሌሎች እንደ ኢነካቶይቭና ኢንዳፎሊግላይት የመሳሰሉ አደገኛ በሽታዎችን ከሰው ወደ ሰው በቀላሉ ሊያስተላልፉ ይችላሉ፡፡ የፀጉር ቤት ማሽኖችን ለማፅዳት በአብዛኛው በጥቅም ላይ የሚውለው አልኮል፣ በሽታ አምጪ የሆኑ ባክቴሪያዎችን ከማሽኑ ላይ በማስወገድ ረገድ የሚኖረው አስተዋፅኦ እጅግ ውስን ነው፡፡ ለፅዳት
የሚውለው አልኮል ሁለት አይነት ነው፡፡ ኢታኖል የተባለው የአልኮል አይነት 70% የሚደርስ ጀርሞችን የመግደል አቅም ሲኖረው ይህ ተግባራዊ የሚሆነው ግን  ማሽኑ በአልኮሉ ከተጠረገ በኋላ ለሁለት ደቂቃ ያህል ጠንከር ያለ ኃይል ባለው ሙቀት ውስጥ እንዲቆይ ሲደረግ ብቻ ነው፡፡ ሌላው
የአልኮል አይነት አይቶፕሮፕላን የሚባለው ሲሆን ይህ የአልኮል አይነት ከኢታኖል የተሻለ ጀርሞችን
የማጥፋት አቅም ያለው ነው፡፡ ይሁን እንጂ አስተማማኝ የሚሆነው መሳሪያው በኃይለኛ የሙቀት ኃይል ውስጥ መቃጠል ሲችል ብቻ ነው፡፡ ከእነዚህ ሌላ ግሎሮግዜኖል፣ ፓበዲን፣ ሃፖክሎራትና ቤንዞልኮሊሎራይድ የተባሉት ኬሚካሎች ጀርሞችንና ባክቴሪያዎችን አስተማማኝ በሆነ ሁኔታ ለማስወገድ የሚችሉ ናቸው፡፡ የፀጉር ቤት ማሽኖች ማበጠሪያዎችና ፎጣዎች በእነዚህ ኬሚካሎች በአግባቡ ሊፀዱና ከባክቴሪያ ነፃ ሊሆኑ ይገባል፡፡ ይህንን ማድረግ በማይቻልባቸው ሁኔታዎች ሰዎች በራሳቸው ማበጠሪያና ፎጣ እንዲጠቀሙ፣ አሊያም ከአገልግሎት በኋላ ማስወገድ በሚቻል ነገር እንዲጠቀሙ ማድረግ ተገቢ ነው” ብለዋል የህክምና ባለሙያው፡፡ በዚህ መንገድ ንፅህናቸው ባልተጠበቁ ፎጣዎችና መሳሪዎች መጠቀሙ ለከፋ የጤና ጉዳትና ኤችአይቪ ኤድስን ጨምሮ እንደ ኤፒታይተስ ቢ ላሉ እጅግ አደገኛ ለሆኑ ተላላፊ በሽታዎች
ሊያጋልጥ ይችላልና ጥንቃቄ ማድረጉ ተገቢ መሆኑን ዶክተር አብርሃም አስገንዝበዋል፡፡ እናም
በወንዶች ጸጉር ቤቶች ማማር ብቻ ሳይሆን በሽታ መሸመትም እንዳለ አውቆ ጥንቃቄ መውሰድ ተገቢ ነው እላለሁ፡፡ ፀጉር ቤቶችም ለደንበኞቻቸው ጤንነት ለይምሰል ሳይሆን ከልባቸው አስበው ተገቢውን የንፅህና አጠባበቅ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ በኃላፊነት የሚያስጠይቃቸው መሆኑንም ማወቅ አለባቸው፡፡  

Published in ዋናው ጤና

ኬሊ የስምንት አመት ታዳጊ ነች፡፡ ወደ ሆስፒታል የገባችው የልብ ዝውውር ቀዶ ጥገና (ትራንስፕላንት) ለማድረግ ነው፡፡ የተቀየረላት ልብ የተወሰደው ደግሞ አንዲት በሰው ከተገደለች የ10 ዓመት ልጅ ነበር፡፡ ኬሊ የተሳካ የልብ ዝውውር አድርጋ ከሆስፒታል ከወጣች በኋላ ግን ህይወቷ በአስፈሪ ህልሞች ተዘበራረቀ። በህልሞቿ የምታየው ደግሞ ልብ የሰጠቻትን የ10 ዓመት ልጅ ገዳይ ነበር። የኬሊ አስጨናቂ ህልሞች እውን መሆናቸው የተረጋገጠው ግን እናቷ ወደ ስነልቦና ባለሙያ ከወሰደቻት በኋላ ነው፡፡ እስከዚህ ቅጽበት ድረስ የልብ ሰጪዋ የ10 ዓመት ታዳጊ ገዳይ አይታወቅም ነበር። ነገር ግን የኬሊ የሌሊት ህልሞች ተሰባስበው ስለገዳዩ አስገራሚ መረጃዎችን ሰጡ፡፡ ጊዜውን፣ መሳሪያውን፣ ቦታውንና የገዳዩን ልብስ ሳይቀር የኬሊ ህልሞች አጋለጡ። በመሆኑም ፖሊስ በዚህ መረጃ ተንተርሶ ገዳዩን በቀላሉ አድኖ በመያዝ ለፍርድ ሊያቀርበው ቻለ፡፡
በሜይ 29፣ 1988 ዓ.ም ክሎር ሲልቪያ የምትባል አንዲት አሜሪካዊት በያሌ ሆስፒታል ውስጥ የልብ ዝውውር ተደረገላት፡፡ ልቡ የተሰጣት እዚያው አሜሪካ፣ ማይን ውስጥ ከሚኖር የ18 ዓመት ወጣት ነበር፡፡ ይህን ጨምሮ በሞተር ሳይክል አደጋ እንደሞተም ለሲልቪያ ተነግሯታል፡፡ ሲልቪያ ቀዶ ጥገና ካደረገች ከቀናት በኋላ ግን ያለ ልማዷ ቢራ የመጠጣት ፍላጐት እንዳደረባት ተናገረች፡፡ ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ልትቆጣጠረው ያልቻለችው የዶሮ ስጋ አምሮት አሰከራት፡፡ በዚህ ምክንያት KFC የተባለው የዶሮ ሬስቶራንት ማዘውተር ጀመረች፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የማትወደውን ቆስጣ መብላትና ቲም ኤስ ስለተባለ ግለሰብ ዘወትር ህልም ታይ ነበር። ሲልቪያ ራሷ ባደረገችው ጥረትና ማይን ውስጥ በሚታተም ጋዜጣ አማካኝነት እየተረዳች ልብ የሰጣት ሰው ቲም እንደሚባል አረጋገጠች፡፡ የቲም ቤተሰቦችን ከተዋወቀች በኋላ፤ ልብ የሰጣት ቲም የዶሮ ስጋ፣ ቆስጣና ቢራ እንደሚወድ አወቀች። በኋላ ላይ ሲልቪያ ይህንን ጨምሮ አጠቃላይ ታሪኳን “A Change of Heart” በሚል መጽሐፍ አሳተመችው። የልብ ዝውውር የተደረገላቸው በርካታ በሽተኞች ከልብ ተከላ በኋላ አጠቃላይ ሰብዕናቸው፣ ባህሪያቸው፣ ፍላጐታቸውና አመጋገባቸው እንደተቀየረ ራሳቸው መስክረዋል፡፡ በቬና ዩኒቨርስቲ ሆስፒታል ውስጥ የቀዶ ጥገና ክፍል ሐላፊ የሆኑት ዶ/ር ቤንጃሚን በንዝል እንደተናገሩት፤ 47 የልብ ተከላ ካደረጉ ህሙማን ውስጥ 15 በመቶ የሚሆኑት ሰብዕናቸው ተቀይሯል፡፡ በቅርብ የተደረጉ ጥናቶች ደግሞ ከሶስት ህሙማን መካከል አንዱ የልብ ተከላን እንደሚፈራ ጠቁመዋል፡፡ በ1999 ዓ.ም አንዲት እንግሊዛዊት ወጣት እሷ ሳትፈልግ በዶክተሮችና በቤተሰቦቿ አማካኝነት ልብ ተከላውን እንድታደርግ መገደዷ ተገልጿል፡፡ የልጅቱ እንቢተኝነት የመነጨው ደግሞ በልብ ዝውውሩ ምክንያት የራሷን ማንነት እንዳታጣ ከመፍራት ነበር።
በልብ ተከላ ታሪክ ውስጥ በጣም አስገራሚ የሆነው የአሜሪካዊው ሶኒ ግራሐም ነው፡፡ ግራሐም የሌላ ሰው ልብ እንደሚያስፈልገው በዶክተሮች ከተነገረው በኋላ፣ ቴሪ ኮተል ከተባለ ራሱን በሽጉጥ ካጠፋ ግለሰብ ልብ ተወስዶ ተተከለለት፡፡ ግራሐም በ1995 ዓ.ም የልብ ተከላውን ቀዶ -ጥገና ካደረገ በኋላ ልብ ከሰጠው ኮተል ሚስት ጋር ተገናኘ፡፡ ግራሐም፣ ቼርሊ ከተባለችው የኮተል ሚስት ጋር በፍቅር ስለወደቀ እርሷን አግብቶ መኖር ጀመረ። ከ12 ዓመታት በኋላ ግን ግራሐም ልክ እንደ ኮተል ራሱን በሽጉጥ አጠፋ፡፡ የሚያስገርመው ግን ቼርሊ ለሁለተኛ ጊዜ የህይወት አጋሯን ማጣቷ ሳይሆን፣ ልብ የተቀያየሩት ሁለቱ ባሎቿ ራሳቸውን በተመሳሳይ መንገድ አጥፍተው መሞታቸው ነበር፡፡ የብሪታንያው “ዴይሊ ሜል” ጋዜጠኛ በአንድ ወቅት እንዲህ የሚል ታሪክ ዘግቦ ነበር፡፡ በጣም ደካማ ክህሎት የነበረው ዘገምተኛ ማናጀር ከሌላ ሰው ልብ ተወስዶ ከተተከለለት በኋላ ድንቅ የሚባል የአርት ችሎታን ተጎናፅፏል፡፡ ታሪኩን አስገራሚ ያደረገው ደግሞ ልብ የሰጠው ሰውዬ አርቲስት መሆኑ ከተረጋገጠ በኋላ ነበር፡፡ ይህን የሰብዕና መለዋወጥ በተመለከተ በርካታ ሀኪሞች የተለያዩ አስተሳሰቦችን አንፀባርቀዋል፡፡ አንዳንድ የስነ ልቦና ባለሙያዎች የተቀየረው ልብ “አንድ አካል” መሆኑን መርሳት የለብንም ይሉናል፡፡ ይህ አካል (ልብ) በሰጪው ሰውዬ ውስጥ ከሚገኙ ማንኛውም አካል በላይ የሳይኪክ ኢነርጂን የያዘ ነው። ባዮሎጂ ባለሙያዋ ሊያል ዋትሰን እንደምትለው የሰውነት ክፍላችን አንዱ አካል የሆነው ልባችን፤ የባህሪያችንን አሻራና ስሜታችንን የያዘ ነው፡፡ ሊያል ዋትሰን ጨምራ ስትናገር፤ ከኛ ጋር ንክኪነት ያላቸው የሰውነት ክችሎቻችን በሙሉ ባህሪያችንን የሚይዙበት እድል አላቸው፡፡
ብዙዎቹ የህክምና ሰዎችና የስነ - ልቦና ባለሙያዎችን ያስማማው ግን “ሴሉላር ሜሞሪ” የሚለው ነው፡፡ ሴሉላር ሜሞሪ ራሱን የቻለ ፅንሰ - ሐሳብ ሲሆን ሰብዕናችንንና ማስታወሻዎቻችንን መዝግቦ የሚይዘው አእምሯችን ብቻ አይደለም ይላል፡፡ ማስታወስ ራሱን የቻለ ሒደት እንደመሆኑ መጠን በሌሎች የሰውነታችን ሲስተሞች ውስጥም ሊፈጠር ይችላል፡፡ በተለይ ደግሞ እንደ ልባችን ያሉ የሰውነት ክፍሎች የአእምሮ ተግባር የሆነውን ማስታወስን በውስጣቸው ሊይዙ ይችላሉ ይላል - የሴሉላር ሜሞሪ ፅንሰ - ሐሳብ፡፡ በእርግጥ ይህ ፅንሰ ሐሳብ አዲስ አልነበረም። በምናባዊ የስነ ጽሑፍ ስራዎቹ የሚታወቀው ማውሪስ ሬናርድስ፣ በ1800ዎቹ ዓ.ም የሴሉላር ሜሞሪ ፅንሰ ሐሳብን በልቦለዱ ውስጥ አንፀባርቋል። በእርግጥ የሬናርድስ አስተሳሰብ፣ እንደ እግርና እጅ ባሉ የውጭ አካሎቻችንም የሴሉላር ሜሞሪ ፅንሰ - ሐሳብ ይሰራል ባይ ነው፡፡ ሬናርድስ “Les mains d’orac” በተባለው ልቦለዱ ውስጥ አንድ የፒያኖ ተጨዋች ገፀ ባህሪ ይገኛል፡፡ ይህ ሰው አንድ እጁን ካጣ በኋላ የሌላ ሰው እጅ ተገጠመለት። የተገጠመለት እጅ ገዳይ ከነበረ ሰው የተወሰደ በመሆኑ ፒያኖ ተጨዋቹም ሰው የመግደል ዝንባሌን ሲያሳይ ሬናርድስ በልቦለዱ ውስጥ አሳይቷል፡፡ በእርግጥ ይህ ታሪክ እኛ ከላይ ከጠቀስናቸው እውነተኛ ታሪኮች ጋር የሚመደብ ባይሆንም (ልቦለድ በመሆኑ) ሴሉላር ሜሞሪን በቀላሉ ለመግለፅ ተስማሚ ሊሆን ይችላል፡፡ አብዛኞቹ የሴሉላር ሜሞሪ ጥናቶች በሳይንቲስቶች የተረጋገጡ ናቸው፡፡ ነገር ግን ብዙዎቹ ሆስፒታሎች የልብ ሰጪዎችን  ቤተሰቦች በመደበቃቸው አብዛኛዎቹ ታሪኮች ምስጢር ሊሆኑ ችለዋል፡፡ ታሪኮቹ ቢገኙ እንኳን ስምና አድራሻቸው አብረው አልሰፈሩም፡፡ በዘመናዊ የህክምና አለም ውስጥ ልብን ጨምሮ ሌሎችን የሰውነት ክፍሎች ከአንዱ ሰው ወደ ሌላው ማዘዋወር የተለመደ ተግባር ሆኗል፡፡ ልክ ከላይ እንደጠቀስናቸው አይነት ታሪኮች፣ አሁንም ቢሆን ቀዶ ጥገና አድርገው የሚነሱ በርካታ ህሙማን የተለየ ባህሪ፣ ጣዕም፣ አስተሳሰብና ሌሎች እንግዳ ሰብዕናን እንደሚያንፀባርቁ በሴሉላር ሜሞሪ ጥናት ተደርሶበታል። ይህ ደግሞ ህክምናው ከሞት ሊያድን ይችል ይሆናል እንጂ ተፈጥሯዊ አለመሆኑን ይጠቁማሉ፡፡ በተጨማሪም የእያንዳንዱ ሰው የሰውነት ክፍል የራሱ ባህሪ፣ ሰብዕና እና ስሜት እንዳለው ከማረጋገጡ በላይ የሁሉም ሰው የሰውነት ክፍሎች የተፈጠሩት በልካችን ተሰፍተው መሆኑን ይጠቁማሉ፡፡
በአንድ ወቅት ከአንድ ሚሊዮን ሰዎች የተሰበሰበው የጣት አሻራ አንድም መመሳሰል እንደሌለው ተገልፆ ነበር፡፡ አንድ ሚሊዮን ሰዎች፣ አንድ ሚሊዮን የተለያየ የጣት አሻራ እንዳላቸው ስንመለከት ማንም፣ ማንንም እንደማይመስል እንገነዘባለን፡፡ የልብ ተከላ ታሪኮችም የሚናገሩት ሁሉም ሰው የራሱ የሆነ የልብ አሻራ እንዳለው ነው፡፡ በእርግጥ ታሪኮቹ ያስተማሩን ትልቁ ነገር በልቦቻችን ውስጥ ትንንሽ አእምሮዎች መኖራቸውን ቢሆንም በሌላ በኩል ደግሞ ከልብ ተከላ በኋላ የሚከሰቱት የባህሪ ለውጥና የሰብዕና መዘበራረቅ መንስኤ፣ ምናልባት የሰዎች ትክክለኛ የልብ አሻራ ተወግደው በምትኩ የማይመለከታቸው አሻራዎች በመግባታቸው ይሆናል፡፡ ዋናው ቁምነገር ግን ልባችን የራሱ አእምሮ እንዳለው መገንዘባችን ነው። የሐገሬ ሰው “ይሄ ልበ ቢስ!” የሚለው ቀደም ብሎ የሴሉላር ሜሞሪ ሳይንስ ገብቶት ይሆን? - ሰላም!!

Published in ዋናው ጤና

     በኦሮሚያ ክልል በቢሾፍቱ ከተማ አስተዳደር ኢንዱስትሪ መንደር በ36 ሚሊዮን ዶላር ወይም ከ800 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ካፒታል የተገነባው አሐዱክስ ፉድ ፕሮዳክትስ አክሲዮን ማኅበር  የብስኩትና የፓስታ ፋብሪካ ተመረቀ፡፡አሐዱክስ ፉድ ፕሮዳክትስ የኢትዮጵያዊ ኢንቨስተርና የእንግሊዝ ኩባንያ ንብረት ሲሆን፣ በኢትዮጵያ ለ20 ዓመታት የሻይ ምርት በማቀነባበር፣ መድኃኒት በማስመጣት፣ በዘመናዊ እርሻ
ልማት፣ በሪል ኢስቴት፣ በፓኬጂንግና በትሬዲንግ ዘርፎች ተሰማርቶ ሲሰራ የቆየው አሐዱ ኃ.የተ.የግ ኩባንያ፤ በሴፕቴምበር 2013 ኩባንያውን የተቀላቀለው የእንግሊዙ ቫሰሪ ግሎባል ግሩፕ
በሽርክና ያቋቋሙት መሆኑ ታውቋል፡፡ ሊዝ በተገኘ 42 ሺህ ካ.ሜ ላይ የተገነባው የብስኩትና የፓስታ ፋብሪካ፣ በኢጣሊያ ታዋቂ የሆኑ 5 ድርጅቶች ያመረቷቸውና የዘመኑ ቴክኖሎጂ ያፈራቸው መሳሪያዎች የተገጠሙለት ፋብሪካ በዚህ
ሳምንት የተመረቀው በኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት ክቡር ዶ/ር ሙላቱ ተሾመና በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ፕሬዚዳንት ክቡር አቶ ሙክታር ከድር ነው፡፡ በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ ፋብሪካው ከየት ተነስቶ የት እንደደረሰ የገለፁት የአሐዱክስ ፉድ ፕሮዳክትስ የቦርድ አባልና ከቫሳሪ ግሎባል ግሩፕ ጋር የኩባንያው ባለቤት የሆኑት አቶ ሰለሞን
ወንድሜነህ፣በአሁኑ ወቅት ምርት የጀመረው የብስኩት ፋብሪካው እንደሆነ ጠቅሰው የፓስታ ፋብሪካውም ህንፃ ግንባታ ስለተጠናቀቀ በቅርቡ መሳሪያዎች ተገጥመውለት ምርት አንደሚጀምር ገልፀዋል፡፡ የብስኩት ፋብሪካው በቀን 500 ኩንታል ብስኩት የማምረት አቅም ያለው መሳሪያ ተተክሎለት ምርት መጀመሩን የጠቀሱት አቶ ሰለሞን፤ ተመሳሳይ የማምረት አቅም ያላቸው 5 መስመሮች
ይተከላሉ ብለዋል፡፡ የፓስታ ፋብሪካው እያንዳንዳቸው በቀን 900 ኩንታል ፓስታ የማምረት አቅም ያላቸው የማምረቻ መስመሮች እንደሚተከሉና ለሁለቱ ፋብሪካዎች በቀን ከ6, 500 ኩንታል በላይ ማምረት የሚችል የዱቄት ፋብሪካ ለመገንባት ማቀዳቸውን ተናግረዋል፡፡ የፋብሪካው ግንባታ 3 ዓመት መፍጀቱን፣ በአሁኑ ወቅት የተለያዩ ብራንድ ያላቸው ብስኩቶች
እንደሚያመርት፣ በቅርቡ የተለየ ጣዕምና ከፍ ያለ ጥራት ያላቸውን ብስኩቶች ለገበያ እንደሚያቀርብ ልጸዋል፡፡ በቀጣይ 3 ዓመት በሚደረገው የማስፋፊያ ሥራ 150 ሚሊዮን ዶላር
ወይም ከ3 ቢሊዮን ብር በላይ እንደሚፈጅ፣ አሁን ያለው 600 የሰራተኛ ቁጥር 3,000 እንደሚደርስ፣ 80 በመቶ የምርት ግብአት ከአገር ውስጥ እንደሚገኝ የጠቀሱት የቦርድ አባሉ።
የኢንቨስትመንቱ ዕቅድ ሲጠናቀቅ አሐዱክስ፣ ከምስራቅ አፍሪካ አንዱና ቀዳሚው አግሮ ፕሮሰሲንግ እንደሚሆን እናምናለን፡፡ ምርታችንን ለዓለም ገበያ በማቅረብ ለአገራችን የውጭ ምንዛሪ እናስገኛለን ብለዋል፡፡ በተለያዩ የመንግሥት አካላት ድጋፍ አሁን ላሉበት ደረጃ ለመብቃት በመቻላቸው ድጋፍ ደረጉላቸውን አካላት ቢያመሰግኑም፣ ያቀዱት ዓለም አቀፍ ደረጃ ላይ ለመድረስ ችግሮች
እንዳሉባቸው አልሸሸጉም፡፡ የኢንዱስትሪው ዞን ኤሌክትሪክ ማሰራጫ ከፍተኛ መጨናነቅ አለበት።
በዚህ የተነሳ ተደጋጋሚ የኤሌክትሪክ ኃይል መቆራረጥ ችግር እየገጠመን ስለሆነ አስተማማኝ
የኃይል አቅርቦት እንድናገኝ አመራር ይስጥልን ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ ወደ ፋብሪካው የሚያደርሰው መንገድ ከባድ የጭነት ተሽከርካሪዎች በሚያደርጉት ምልልስ እየተበላሸና ችግር ስለፈጠረባቸው ቀደም ሲል የክልሉ መንግስት ፕሬዚዳንት አቶ ሙክታር፤ ፋብሪካውን በጎበኙበት ወቅት መንገዱ አስፋልት ይለብሳል በማለት የገቡትን ቃል እየተጠባበቁ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ እንዲሁም ፋብሪካቸው የሚገኘው በአግሮ ፕሮሰሲንግ ዞን ቢሆንም የኢንዱስትሩ ውጤት አምራች ፋብሪካዎች ቦታ ተሰጥቷቸው ምርት መጀመራቸውን ጠቅሰው ይህ ስብጥር ዓለም አቀፍ የምግብና ድራግ ቁጥጥር ሰርቲፊኬት ለማግኘት የምናደርገውን ጥረት ይፃረራል፡፡ ስለዚህ ፋብሪካዎቹ የሚፈጥሩት ብክለት፣ ለውጭ ገበያ በምናቀርበው ምርት ላይ
ከፍተኛ ተፅዕኖ ስለሚፈጥር ብክለቱ የሚወገድበት መንገድ በአፋጣኝ እንዲፈልጉ የክልሉን
መንግስትና የከተማ አስተዳደሩን ጠይቀዋል፡፡ ፋብሪካው ዓለም አቀፍ ብቃቱ የተረጋገጠ የምግብ ማምረቻ ተቋም መሆኑንና የምግብ ደህንነትን ዋስትና ለማረጋገጥ እየሰራ ነው። ሰራተኞችን ሲቀጥር ያሰለጥናል፣ የሥራ ላይ ሥልጠናም ይሰጣል፡፡ ለሰራተኞቹ መፀዳጃና መመገቢያ ክፍል፣ ቢታመሙ ምርመራ የሚያደርጉበት ላቦራቶሪ፣ ልብስ መቀየሪያ የመሳሰሉ አገልግሎቶች ተገቢውን የጥራት ደረጃ እንደሚያሟሉ ተደርገው ተሰርተዋል፡፡ የሰራተኞቹ ደሞዝ ከሌሎች የምግብ ማምረቻ የፋብሪካዎች ጋር ሲነፃፀር በእጥፍ እንደሚጨምር ቀደም ሲል በናስ ምግብ ፋብሪካ ይሠራ የነበረውና አሁን ፋብሪካው የሺፍት ኃላፊ ገልጿል፡፡ “ሁላችንም በሚከፈለን ደሞዝና በሚደረግልን ክብካቤ ደስተኞች ነን፡፡ ለምሳሌ ብስኩቱን በማሸግ
ሥራ የተሰማሩ ሴቶች ዝቅተኛ ደሞዝ 2000 ብር ነው” ብሏል፡፡ የአሐዱ ኃ.የተ.የግ. ኩባንያ ባለቤቶች አቶ ሰለሞን ወንድሜነህና በላቤታቸው ወ/ሮ ራሔል አሰፋ በፋብሪካው ግንባታ ወቅት የላቀ የስራ አፈፃፀም ላሳዩና ፋብሪካው ለደረሰበት ደረጃ ያበቁትን ሁለት
ሰራተኞች በግል ገንዘባቸው መኪና ገዝተው ሸልመዋል፡፡  ለፕሮጀክት ማናጀሩ ለአቶ እሱባለው ከፈለ በ900ሺህ ብር የቤት አውቶሞቢል ገዝተው ሸልመዋል፡፡ ለፕሮጀክት አስተባባሪው ለአቶ ገሠሠ አይኛው 1.7 ሚሊዮን ዋጋ ያለውን ፒክአፕ መኪና ቁልፍ አበርክተዋል፡፡ ኩባንያው ማኅበራዊ ኃላፊነቱን መወጣት ከአሁኑ የጀመረ ሲሆን፣ ለአካባቢው አርሶ አደሮች ከብት ውሃ ማጠጫና ለመስኖ አገልግሎት የሚውል ውሃ ማጠራቀሚያ በመገንባት በዕለቱ አስመርቋል። የትምህርት ጥራትን ለማበረታታት ከፍተኛ ነጥብ ያመጡ ተማሪዎችን ምስል የሚይዝ አደባባይ በቢሾፍቱ ከተማ እያስገነባ ሲሆን ለእነዚህ ስራዎች ከ6 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ ማድረጉ ታውቋል፡፡

       የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የዘጠኝ ወር የዕቅድ አፈጻጸሙን ለመገምገም ከሚያዝያ 15-17 በባህርዳር
ከተማ ባደረገው ስብሰባ የአፈጻጸም ክንውኑ አጥጋቢ እንደነበር አስታወቀ፡፡ ባለፉት ዘጠኝ ወራት የተቀማጭ ሂሳብ ዕድገትን ለማሳደግ ባደረገው እንቅስቃሴ 27.5 ቢሊዮን ብር
ተጨማሪ ተቀማጭ ማሰባሰቡን አመልክቷል፡፡ ይህም ካለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነፃፀር
የተሻለ መሆኑንና የባንኩ ጠቅላላ ተቀማጭ ሰኔ 30 ቀን 2006 ከነበረበት 139.3 ሚሊዮን  ብር ወደ 220.8 ቢሊዮን ብር ከፍ ማለቱን አመልክቷል፡፡ የባንክ አገልግሎትን ተደራሽ ከማድረግ አኳያ በዘጠኝ ወር እንቅስቃሴው 107 አዲስ ቅርንጫፎች
በመክፈት፣ የቅርንጫፎቹን ጠቅላላ ቁጥር 939 ማድረሱን፣ ከአዳዲስ ደንበኞቹ 1.1 ቢሊዮን ብር ተቀማጭ ገንዘብ ማሰባሰቡን፣ የ1.9 ሚሊዮን አዳዲስ ደንበኞች ሂሳብ በመክፈቱ የአስቀማጮች ጠቅላላ ብዛት 10.1 ሚሊዮን መድረሱን አስታውቋል፡፡
ባለፉት ዘጠኝ ወራት የውጭ ምንዛሪ ለማሰባሰብ ባደረገው ጥረት ከተለያዩ ምንጮች 4.4 ቢሊዮን
ዶላር ማሰባሰቡን ጠቅሶ፣ ከዚህ ውስጥ 3.63 ቢሊዮን ዶላር በውጭ ከሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የተላከ መሆኑንና ቀሪው 756.1 ሚሊዮን ዶላር ከወጪ ንግድ መገኘቱን
አመልክቷል፡፡ አዳዲስ ብድሮች ለመስጠትና ብድሮችን ለማስገባት ባደረገው ጥረት፣ 62.9 ቢሊዮን ብር ለብድርና ለቦንድ ሽያጭ አቅርቦ፣ 28 ቢሊዮን ብር ከብድር መሰብሰብ መቻሉን ገልጿል፡፡ ወደ ጥሬ ገንዘብ አልባ የግብይት ሥርጭት ለመሸጋገር በሚያደርገው እንቅስቃሴ የባንክ ካርድ፣
የሞባይልና ኢንተርኔት የባንክ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆን አስፈላጊ ነው፡፡ በዚሁ መሰረት ንግድ ባንክ በተከላቸው 627 ኤቲኤም ማሽኖች በተደረጉ 11.1 ሚሊዮን ግብይቶች 9.6 ቢሊዮን ብር መገኘቱንና ከ33 ሚሊዮን ዶላር ጋር የሚመጣጠን የውጭ ምንዛሬ ልውውጥ መደረጉን አስታውቋል፡፡ በተለያዩ የገበያ ቦታዎች 1,162 POS ማሽኖች በማስቀመጥ 553.1 ሚሊዮን ብር ዋጋ ያላቸው
228,903 ግብይቶች መደረጋቸውን፣ በአሁኑ ወቅት በደንበኞች እጅ ከሚገኙ ካርዶች 654, 641 አገልግሎት እየሰጡ መሆኑን፣ ለሞባይል ባንኪንግ ከተመዘገቡት ውስጥ 144,588 ደንበኞች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆናቸውን፣ የሞባይል ባንኪንግ ተጠቃሚዎች 39 ሚሊዮን ብር የሚያወጡ 9,877 ግብይቶች መፈፀማቸውን፣ በሞባይል ባንኪንግ 49,728 ግብይቶች ተደርገው 173.3 ሚሊዮን ብር ማስተላለፍ መቻሉን፣ በአሁኑ ወቅት 1,127 የኢንተርኔት ባንክ ተጠቃሚ ደንበኞች ማፍራት መቻሉንና በኢንተርኔት ባንክ በተከናወኑ 5,895 ግብይቶች 42.5 ሚሊዮን ብር ማስተላለፉን አብራርቷል፡፡ የባንኩ አዳዲስ የባንክ አገልግሎቶች አፈጻጸም ስንመለከት፣ ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት 69,217 ሂሳቦች ተከፍተው 807 ሚሊዮን ብር መቀመጡን፣ በሴቶች ልዩ ቁጠባ 422,482 ደንበኞች ተመዝግበው ያስቀመጡት ገንዘብ 3 ቢሊዮን ብር መድረሱንና በታዳጊዎች የቁጠባ ሂሳብ 273,560 ወጣቶች ተመዝግበው 353 ሚሊዮን ብር መቆጠባቸውን አስታውቋል፡፡ ንግድ ባንክ ባለፉት ዘጠኝ ወራት 4,312 አዳዲስ ሰራተኞች የቀጠረ ሲሆን የሰራተኞቹ ጠቅላላ ብዛት 22,475 መድረሱን፣ የባንኩ ጠቅላላ ሀብት 276.3 ቢሊዮን ብር መሆኑን፣ በዘጠኝ ወር ውስጥ ጠቅላላ ገቢው 15.9 ቢሊዮን መድረሱንና በዚሁ ጊዜ ከታክስ በፊት 9.05 ቢሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን አስታውቋል፡፡  

የአለም የጤና ድርጅት ባወጣው መረጃ በአለማችን ላይ እድሜያቸው ከ15-49 የሆነ 340/ ሚሊዮን
ሰዎች በመራቢያ አካላት ኢንፌክሽን እንዲሁም በተለያዩ የአባላዘር በሽታዎች እንደሚያዙ ቁሟል። ይህ የመራቢያ አካላት ኢንፌክሽን እንደኛ ባሉ ታዳጊ ሀገራት ትልቁን ቁጥር የሚሸፍን የስነተዋልዶ ጤና ችግር እንደሆነም በተለያየ ግዜ የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡የመራቢያ አካላት ልክ እንደ ሌሎች የሰውነት ክፍሎቻችን ሁሉ በተለያየ ግዜ እና አጋጣሚ ተለያዩ በሽታዎች ሊጠቁ ይችላሉ፡፡ በተለያየ ምክንያት የሚፈጠሩ ኢንፌክሽኖች ወይም በህክምናው ሳይንስ RTIs (Reproductive tract infections)  ለዚህ ተጠቃሽ ናቸው፡፡ዛሬው ፅሁፋችን በእነዚህ በመራቢያ አካላት ላይ በሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች እንዲሁም የአባላዘር ሽታዎች ዙሪያ ባለሙያ አነጋግረን ያገኘነውን ምላሽ እንዲህ ልናስነብባችሁ ወደናል፡- ለዛሬ ያነጋገርናቸው ባለሙያ ዶክተር መብራቱ ጀንበር ይባላሉ፡፡ ዶክተር መብራቱ በብራስ የእናቶች እና ህፃናት ሆስፒታል የማህፀንና ፅንስ ሀኪም ናቸው። የምናወራው በመራቢያ አካላት ላይ
በሚከሰቱ ኢንፌክሽኖች ዙሪያ ነውና በአጠቃላይ የስነተዋልዶ አካላት ስንል የትኛውን የሰውነት ክፍል የሚያጠቃልል ነው? ብለን በቅድሚያ ላነሳንላቸው ጥያቄ የሚከተለውን ማብራሪያ ሰጥተውናል፡፡
“...የስነተዋዶ አካል ስንል በሴት በኩል የሴት ብልትን እና የማህፀን ክፍሎችን ባጠቃላይ እንዲሁም ልጅ  ከተወለደ በኋላ ወተት በማመንጨት የሚያገለግሎ ጡቶችንም ይጨምራል፡፡ በወንድ በኩል ደግሞ የወንድ ልጅ ብልት አለ የዘርፍሬዎች እንዲሁም ሌሎች ሆርሞን በማመንጨት የሚያገለግሉ እጢዎች አሉ፡፡ እነዚህ በሙሉ ከስነተዋልዶ ጋር  ቀጥተኛ የሆነ ግንኙነት ያላቸው የሰውነታችን ክፍሎች ናቸው፡፡” የስነተዋልዶ አካላትን የሚያጠቁ ኢንፌክሽኖች በብዛትም ሆነ በአይነት እጅግ በርካታ ሲሆኑ በእነዚህ የሰውነት ክፍሎች ላይ በሚፈጠር ባክቴሪያ መንስኤነት የሚከሰቱ እና በግብረስጋ ግንኙት አማካኝነት የሚተላለፉ የአባላዘር በሽታዎች በሚል በሁለት እንደሚከፈሉ ባለሙያው ይናገራሉ፡፡ “...የስነተዋልዶ አካላትን የሚያጠቁ የኢንፌክሽን አይነቶች በጣም ብዙ ናቸው ነገር ግን በዋናነት በሁለት ከፍለን ልናያቸው እንችላለን፡፡ አንደኛው በጥገኛ ህዋስ ወይም ባክቴሪያ አማካኝነት የሚመጣ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ በግብረስጋ ግንኙነት የሚተላለፉ የበሽታ አይነቶች ወይንም sexually  transmitted infections ተብለው የሚጠሩት ናቸው፡፡”ምንም እንኳን ሁሉም አይነት ኢንፌክሽኖች የተለያየ የጤና ችግር የሚያስከትሉ ቢሆንም ትልቁ ትኩረት መሰጠት ያለበት በግብረስጋ ግንኙት አማካኝነት ሊተላለፉ የሚችሉት የበሽታ አይነቶች ላይ ነው ይላሉ ዶክተር መብራቱ፡፡ ለዚህም በምክንያትነት የሚያነሱት እነዚህኞቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ብዙውን የህብረተሰብ ክፍል የሚያጠቁ እና በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት ተላላፊ መሆናቸውን ነው፡፡ ስለዚህም ይላሉ ዶክተር፡-
“..ስለዚህ sexually transmitted infections  ወይንም በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት ሊተላለፉ የሚችሉ የበሽታ አይነቶች የትኞቹ ናቸው? እንዴትስ መከላከል ይቻላል? በሚሉት ጉዳዮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ መስራት እና በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ መፍጠር ያስፈልጋል፡፡”አንዳንዶቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ከማህፀን ውጨኛው ክፍል አንስቶ በተለያዩ የማህፀን ክፍሎች ላይ ሊዛመቱ የሚችሉ ሲሆን በማህፀን ውጫዊ ክፍል ላይ ብቻ ተከስተው በህክምና ክትትል ወዲያው ሊጠፉ የሚችሉም አሉ፡፡  “...vulval area ወይንም ደግሞ የብልት የውጨኛውን ክፍል ሊያጠቁ የሚችሉ ወይም ቆዳው ላይ ብቻ የሚወጡ አንዳንድ ኢንፌክሽኖች አሉ፡፡ ነገር ግን ከእነዚህ የውጪውን አካል ከሚያጠቁ ኢንፌክሽኖች መካከል የውስጠኛውን ክፍልም ሊያጠቁ የሚችሉ ይኖራሉ፡፡ ለምሳሌ ፈንገስ የምንለው የውጪውን ክፍል ከማሳከኩ እና ከማቅላቱ በተጨማሪ የውስጠኛው ክፍል ላይም ከፍተኛ የሆነ የማሳከክ ስሜት ያመጣል፡፡ በተጨማሪም ነጭ የሆነ አይብ የመሰለ ፍርፍር የሚል አይነት ፈሳሽ ይኖረዋል፡፡ ይህ በብዛት የሚከሰት የፓራሳይት አይነት ሲሆን በተለይ በእርግዝና ሰአት በጣም ይበዛል፡፡     በተቃራኒው ደግሞ በውስጠኛው የማህፀን ክፍል ላይ የሚከሰቱ የኢንፌክሽን አይነቶችም  አሉ፡፡ ለምሳሌ የግብረ ስጋ ግንኙነት በመልካም ሁኔታ እንዲካሄድ ሊያደርጉ የሚችሉ እርጥበት የሚያወጡ እጢዎች መውጫ በር ላይ የሚፈጠሩ የኢንፌክሽን አይነቶች አሉ። በዚህም ምክንያት የፈሳሽ መውጫ ቀዳዳው ይጠባል ወይም ይዘጋል፡፡ ይህም በብልት አካባቢ እብጠት ለሚያመጣው Bartholin’s cyst ወይም Bartholinitis  ለሚባለው ኢንፌክሽን መፈጠር ምክንያት ይሆናል፡፡”ሌሎች በቫይረስ አማካኝነት  የሚተላለፉ የኢንፌክሽን አይነቶችን ሲያብራሩም፡-  “ሌሎች ልክ እንደ chancroid, wart  ወይም ደግሞ papillomavirus  ወይም ኪንታሮት በመባል የሚጠራው አይነት  በቫይረስ አማካኝነት የሚተላለፉ  ኢንፌክሽኖች አሉ፡፡ እንዲሁም ደግሞ Herpes zoster  ወይም ደግሞ Herpes simplex የሚባል አለ፡፡ ይህም በቫይረስ የሚተላለፍ ሲሆን የብልት ውጨኛውን አካባቢ ያቆስላል፡፡” በባክቴሪያ አማካኝነት ከሚከሰቱት ይልቅ በግብረስጋ ግንኙነት አማካኛነት የሚመጡት ኢንፌክሽኖች  በይበልጥ ወንዶችን ያጠቃሉ ይላሉ ዶክተር መብራቱ፡፡
“...በወንዶች ላይ ባክቴሪያል ኢንፌክሽን የተለመደ አይደለም፡፡ ነገር ግን ወንዶች በግብረስጋ አማካኝነት በሚተላለፉ የኢንፌክሽን አይነቶች በብዛት ሲጠቁ ይስተዋላል፡፡ በተለይ Gonorrhea እና syphilis,  የምንላቸው የአባላዘር በሽታዎች ዋነኞቹ ናቸው። በተጨማሪም ከርክር ወይም chancroid, wart  እንዲሁም ደግሞ papillomavirus     የምንላቸውም ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡”በፈረንጆቹ 2008 በናይጄሪያ የተደረገ አንድ ጥናት የግብረ ስጋ ግንኙነት እንዲሁም ደካማ የሆነ የንፅህና አጠባበቅ 44.6% የሚሆነውን የበሽታው መተላለፊያ መንገድ እንደሚይዝ ጠቁሟል፡፡“...መተላለፊያ መንገዱ አብዛኛውን ግዜ የሰውነት አቅም መድከም ነው፡፡ በተጨማሪም ከፍተኛ የጣፋጭ ይዘት ያላቸው ምግቦች ወይም መጠጦች ማዘውተር እና አብዝቶ መጠቀም በሽታው የሚኖረውን ተጋላጭነት ሊጨምር ይችላል፡፡ እንዲሁም አዘውትረው ብልታቸውን የሚታጠቡ ሴቶች ይህ ችግር ሊያጋጥማቸው ይችላል። የብልት ተፈጥሯዊ እርጥበት ታጥቦ መወገድ የለበትም
ምክንያቱም ብልት የእራሱ የሆነ በሽታ ተከላካይ ፈሳሽ አለው፡፡ ይህ መከላከያ ደግሞ አላስፈላጊ
ፓራሳይቶችን ያጠፋል፡፡ ስለዚህ የብልት አካባቢ ቢያንስ በቀን ሁለት ግዜ ጠዋትና ማታ ከታጠበ በቂ ነው፡፡ ሌሎቹ የኢንፌክሽን አይነቶች ደግሞ ቀደም ሲል እንደ ገለፅኩት በግብረስጋ ግንኙነት አማካኝነት የሚተላለፉ     ናቸው፡፡ ለዚህም እንደ Gonorrhea, syphilis, Trichomoniasis እንዲሁም papillomavirus የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላ፡፡” አብዛኞቹ በባክቴሪያ አማካኝነት የሚመጡት ኢንፌክሽኖች ከግል ንፅህና ጉድለት ወይም ተገቢውን የንፅህና አጠባበቅ ባለመከተል የሚከሰቱ መሆናቸውንም ጨምረው ይገልፃሉ፡-
“ከሰገራ ጋር የሚወጡ በጣም አጥቂ የሆኑ ህዋሳቶች አሉ በጣም በብዛት የሚገኘው Escherichia coli  ወይም E. coli  የምንለው  የባክቴሪያ አይነት ነው፡፡ ይህ ባክቴሪያ በማህፀን አካባቢ ሲገኝ የማህፀን ኢንፌክሽን እንዲሁም የሽንት መተላለፊያ ቱቦ ኢንፌክሽኖችን ያመጣል፡፡ ስለዚህ በተቻለ መጠን የግል ንፅህና አጠባበቅ ስልቱን ማወቅ ያስፈልጋል ወይም ደግሞ የጤና ባለሙያ ጋር በመሄድ እንዴት ባደርግ ነው እነዚህን ኢንፌክሽኖች መከላከል የምችለው የሚለውን በተመለከተ የምክር አገልግሎት መቀበሉ በጣም ጥሩ ይሆናል፡፡” የዚህ አይነት የስነ ተዋልዶ ጤና ችግሮች ተገቢው ህክምና ካልተደረገላቸው ለመሀንነት፣ ከመሀፀን ውጪ ለሚፈጠር እርግዝና ብሎም ለኤች አይቪ ቫይረስ የማጋለጥ እድላቸው ከፍተኛ ነው፡፡ ችግሩ እየተባባሰ ከሄደም ለሞት መዳረጋቸው አይቀሬ ነው ብለዋል ዶ/ር መብራቱ ጀምበር፡፡ “...እነዚህ ኢንፌክሽኖች እስከ ሞት ደረጃም ሊያደርሱ ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም ኢንፌክሽኑ ሀይለኛ እየሆነ በሄደ ቁጥር ወደ ሌሎች የሰውነታችን ክፍሎች መዛመቱ አይቀርም፡፡ ሌላው ያልጠቀስነው ደግሞ ኤችአይቪም ነው፡፡ ኤች አይቪም እንደዚሁ በግብረስጋ ግንኙነት ነው።  ምንም እንኳን የግብረስጋ ግንኙነት ብቻ የመተላለፊያ መንገዱ ባይሆንም በግብረስጋ ግንኙነት የመተላለፍ ሀይሉ ከፍተኛ ነው፡፡ ስለዚህ ችግሩ እየጠና ሲሄድ     ህክምና በወቅቱ ካልተገኘ የመሞት አጋጣሚም ይኖራል።”

Published in ላንተና ላንቺ

     ስለ ገጣሚነቱ እርግጠኛ ነው፡፡ ገጣሚነትን ከፈጣሪ ያገኘው ፀጋ ነው፡፡ መታገል አስቦ አያውቅም፡፡
በተፈጥሮው ታድሏልና፡፡ ብዙ መጽሐፍት አሳትሟል፡፡ ለምን ስላሳተማቸው መጽሐፍት ሰው ሲወያይ እንደማይሰማ ግን አልገባውም። አምስት አመት ብቻ ነው ያለፈው፣ የመጨረሻውን መጽሐፉን ገበያ ላይ ካዋለ፡፡ እርግጠኛ ነው ስለገጣሚነቱ፡፡ እጣ ፈንታው ነው። እጣ ፈንታው ስሙ በወጣለት ቀን የፀደቀ
ስለመሆኑ እሱም ሆነ አባቱ ያውቃሉ፡፡ ግን መቼ እንደሆነ እርግጠኛ ባይሆንም አንድ ቀን የገጣሚዎች አውራ ተደርጐ የሚሰየምበት ቀን ይመጣል፡፡ አንዳንድ ጊዜ የኮከቡ ጥርሶች ከዘመን ጥርስ ጋር አልገጥም እንደሚል ይገባዋል፡፡ አልገጥም የሚለው ዘመኑ ነው፡፡ የዘመን ጥርስ ግን እጣ ፈንታን የመለወጥ አቅም የለውም።
ይታገለው ይሆናል፡፡ ግን በስተመጨረሻ አይሳካለትም፡፡ የዘመን ጥርስ ወረት ነው፡፡ ወረቱ ሲያልፍ ተሸራርፎ ይወድቃል፡፡ ያኔ የሚቀረው ገጣሚው እና ግጥሞቹ ብቻ ይሆናሉ፡፡ ይህ እምነቱ ነው፡፡ እምነት ብቻ ሳይሆን ለሱ የተፃፈለት እውነቱ ነው፡፡ እንደወትሮው ቀኑን ከዘመኑ ውስጥ መዞ እለት ብሎ ጠራው፡፡ ጠርቶት ከመኝታው ተነሳ፡፡ አድባሩ ከምትሰፍንበት ብቸኛ ስፍራ ነው ውሎው፡፡ ከአዳር በስተቀር ህይወቱ የተሳሰረችው ከዚህ የውሎው ስፍራ ነው፡፡ ስፍራዋ አራት ኪሎ ናት፡፡ አራት ኪሎ ጠዋት ወፍራም ቡናን ትመስላለች ለገጣሚው፡፡ የአራት ኪሎን ማለዳ በቡና ስኒ መስሎ ብዙ ግጥም ጽፏል፡፡ ቡናን አራት ኪሎ፣ አራት ኪሎን ደግሞ ቡና አድርጐ ያገጣጠመው ማነው? ተብሎ ከተጠየቀ መልሱን ማንም ያውቀዋል፡፡ ገጣሚው ነው፡፡ ገጣሚው በፃፋቸው ቅኔዎቹ የተነሳ በአራት ኪሎ በማለዳ ከቡና ውጭ ሲጠጣ የሚገኝ ለምልክት እንኳን አይገኝም፤ ተብሎ የተሞገሰበት ጊዜ ነበር፡፡ እየተሞገሰ ብዙ ከመቆየቱ የተነሳ በራሱ ምስል ስር ገጣሚው ራሱ ተንበርክኮ ኖረዋል፡፡ ጨጓራውን ቢልጠው እንኳን፣ ቡናው እና ስኒው ከድግግሞሽ ብዛት ጣዕማቸውን ማጣታቸው ቢታሰበው እንኳን የማለዳ ተግባሩን ለአንድም ቀን አዛንፎ አያውቅም፡፡
ቡናን መጥላት ግጥሞቹን እንደመጥላት ነው፡፡ አራት ኪሎን ማዘውተር ማቆም ከአድባሯ ጋር መፍታት ነው ብሎ ያምናል፡፡ አዳዲስ እይታ መፍጠር እንደሚጠበቅበት አይክድም፡፡ ግን በፊት ከጠጣው የቡና አተላ ላይ የሃሳብ ቅራሪ እንዴት ማፈንገጥ እንደሚችል እርግጠኛ አይደለም። የተለመደው ካፌ ውስጥ የተለመደው ቦታ ተቀምጦ የተለመደውን የቡና ሲኒ እየጠበቀ በተለመደው መንገድ እግሩን አጣመረ፡፡ ከማጣመሩ በማስከተል ሲጋራውን ለኮሰ፡፡ ሁሉም ተግባሩ የተያያዙ ናቸው፡፡ ከዚሁ የተግባር ሰንሰለት ውስጥ አምስት የግጥም ደቡሎች ፈልቀዋል። የትኛው ግጥም ከየትኛው መድበል ውስጥ እንደወጣ የሚያውቁ ብዙ ተከታዮች እንዳሉት የሚያውቀው እሱ ነው፡፡ እውቀቱን ተጠራጥሮ አያውቅም፡፡ ለመጠራጠር የሚያበቃ ምክንያት ገጥሞት አያውቅም፡፡ ግን የዘመኑ ጥርሶች እንደዚህ አይነት ለጥርጣሬ የሚያተጉ ፍጡራንን ትውልድ ብላ እያመጣች መሆኑን አልፎ አልፎ ይጠረጥራል፡፡ በአለፈው አንድ ወጣት (ውርጋጥ) ከእሱ ጐን ተቀምጦ የእሱን ግጥም በሌላ ገጣሚ ስም ሲቀኝ ሰምቶት በገላጋይ ነው ከጠብ የተረፈው፡፡ ሁለተኛ እንዳይለምደው አሳፍሮ ያንን ወጣት ሸኘው፡፡ የሱን ስም ከተቀኘው ግጥም መነጣጠል የብልግና መጀመሪያ መሆኑ ገብቶታል፡፡
ስምን ከግጥም መነጣጠል ሃይማኖትን ከሀገር ከመነጣጠል፣ ማተብን ከአንገት በጥሶ ከመጣል የተለየ አይደለም፡፡ ስሙ እጣ ፈንታው ነው፡፡ ግጥሙ ደግሞ የእጣ ፈንታው ግብ ነው፡፡ እጣ ፈንታ ያለ ግብ ምንም እርባና የለውም፡፡ “አንድ” ከተባለ “ሁለት” መከተሉ አይቀርም። በአራት ኪሎ ላይ እሱ ጐን የተቀመጠው ጐረምሳ የሰራውን ስህተት በሌላ ሰፈር በዚያው ቅጽበት ሌላ ወጣት እየሰራው እንደሆነ ያውቃል፡፡ ማወቁ ለመጀመሪያ ጊዜ ስጋት ፈጠረበት፡፡ እስካሁን በሰራቸው ግጥሞች አንድን ትውልድ ሳይሆን አንድን
ሺ ትውልድን ገዝቶ ማቆየት እንደሚችል ነበር የሚያስበው፡፡ እጣ ፈንታውም የተፃፈው እንደዚያው ተብሎ ስለሆነ ጥርጣሬ ኖሮት አያውቅም ነበር፡፡ ጥርጣሬም አንድ ብሎ ከተጀመረ ሁለት እና ሦስት ሆኖ ራሱን ያበዛል፡፡ ገጣሚው ስለራሱ ቅንጣትም ጥርጣሬ ተሰምቶት ባያውቅም በዙሪያው ያሉት ሰዎች ላይ ተፈጥሮ ከሆነ መመርመር እንዳበት አሰበ፡፡ ሲጋራውን እያጨሰ…ጓደኞቹን መጠበቅ ጀመረ። ቡናውን በሙሉ ጥሞና ለማጣጣም መንፈሱን ሰበሰበ። ግን ምንም አዲስ ነገር የለውም፡፡ ወንበሮቹን…አስተናጋጆቹን አይኑን ጨመቅ እና በልጠጥ እያደረገ ታዘባቸው፡፡ ምንም አዲስ ነገር የላቸውም፡፡ ገጥሞ ጨርሷቸዋል፡፡ ሰዎቹን ሴቶቹን ከአራት ኪሎ ሆኖ የሚታየውን ሰማይ፣ ከአራት ኪሎ የሚታየውን አምላክ…ገነት እና ገሀነም ከአራት ኪሎ
አንፃር ሁሉም ተብለዋል፡፡ የተባለው ደግሞ በእሱ ብቻ ሊባል የሚችል ነው፡፡ የሚሻሻል ነገር የለውም፡፡ እርግጠኛ ነው፡፡ ታዲያ ግጥሙ ያለ እሱ ስም መንቀሳቀስ የጀመረው ምን ሆኖ ነው፡፡ ጓደኞቹ ተንጠባጥበው እንደሚመጡ ያውቃል፡፡ ከበውት እንደሚቀመጡ እና ሙሽራ እንደሚያደርጉትም ያውቃል፡፡ ትላንት የተደረገው ዛሬም ይደገማል፡፡ ዘመናት የእሱን ዝና ሊነኩት አይችሉም፡፡ ከጓደኞቹ መሃል አንደኛው መጣ፡፡ በእጁ አዲስ መጽሐፍ ይዟል፡፡ የግጥም መጽሐፍ ነው፡፡ ከእሱ መጽሐፍ ውጭ አዲስ የግጥም መጽሐፍ ውይይት ሊደረግ መሆኑ ነው፡፡ በውይይቱ ሁሉ ጐልቶ የሚወጣው ሁሌም አንድ እውነት ነው፡፡ የእሱን የመጀመሪያ ግጥም የሚያክል ገጣሚ መጥቶ አያውቅም፡፡ የሱን የግጥም መጽሐፍ የሚያክሉ ግጥሞች በሀገሪቷ ታሪክ ተጽፈው አያውቁም። አምስቱ መጽሐፍት ደግሞ ለዘለአለም በግጥም ዙፋን ላይ ቋሚ ሆነው ነግሰዋል፡፡ የእሱን አሻራ ለመምሰል የሚሞክሩ እንጂ በአሻራቸው አሻራውን ለመብለጥ የሚንደፋደፉ ሁሉ ከውድድሩ
ቀድመው ተሸንፈዋል፡፡ ሁለተኛው ቡናውን አዘዘ፡፡ ጓደኛው በሌላው ነገር ሊሽቀዳደመው ባይችልም በቡና ሲኒ ማንሳት ግን ለመግዳደር ይሞክራል፡፡ ገጣሚው ዘና ብሎ ሁለተኛ ሲጋራ ለኮሰ፡፡ የግጥም ስሜት መፈጠር የሚጀምረው ከሁለተኛው ሲኒ በኋላ ነው፤ በተደጋጋሚ እንዳየው፡፡ ስሜቱ ሲፈጠር በወረቀት ላይ አውጥቶ ይጫጭራል፡፡ የጫረውን አጥፎ ኪሱ ይከታል፡፡ ከዛ ያሰላስላል፡፡ ቡና ይደግማል። በዙሪያው ደቀ መዝሙሮቹ ያለ አንዳች ህውሰት ትንፋሻቸውን ውጠው ይጠብቃሉ፡፡ የፈጀውን ያህል ጊዜ ቢፈጅ በፀጥታ ይጠብቁታል፡፡
የቡና ሰንሰለት፣ በድራፍት ሰንሰለት ለመተካት የመጀመሪያው ትዕዛዝ በገጣሚው ሲሰጥ ስራ መጠናቀቁን ማብሰሩ እንደሆነ ያውቃሉ፡፡ በዙሪያው ያሉት እንደ ንብ እዝዝዝ ማለት ይጀምራሉ፡፡ ገጣሚው ሁሌ ተጋባዥ ነው። ፀሐይ ነው፤ ብርሐኑን እንደማያልቅ አድርጐ፣ ለዘመናት እንዳይደበዝዝ አድርጐ ሰጥቷል፡፡ ስለ
ሌላው ነገር ከዛ በኋላ አያገባውም፡፡ ስለ መብል እና መጠጥ እሱ ማሰብ አይፈልግም፡፡ ሃሳብ ሊሆንባቸው የሚገባ መፍትሔ ያብጁ፡፡ ደግሞም እስከ አሁን አበጅተው ቆይተዋል፡፡ ዛሬ ግን ለመጀመሪያ ጊዜ እየፃፈ ሲንሾካሹኩ ሰማቸው፡፡ እንዳናጠቡት ለማስገንዘብ አንድ ሁለቴ በአይኑ ገሰፃቸው፡፡ እየተቀባበሉ የመጀመሪያው በግ ይዞ የመጣውን መጽሐፍ ያነባሉ፡፡ እያነበቡ እንደነበር በተመስጦው ውስጥም ሆኖ ያውቃል፡፡ በጐቹ ሌላ እረኛ ሊኖራቸው በፍፁም እንደማይችል ያውቃል፡፡ የግጥም ተራ አስከባሪ እሱ ብቻ
ነው። ጉልበቱን አስመስክሯል፡፡ እስከወዲያኛው፡፡ ምን እንደሆነ ጉዳዩን ጠየቃቸው፡፡ የመጽሐፉን ገጽ ገለጥ ገለጥ አድርገው አንድ ስንኝ አነበቡለት፡፡ ድገሙልኝ አላቸው፤ ደገሙለት፡፡ በእዝነ ህሊናው ወደ ራሱ አምስት የግጥም መጽሐፍ ሄዶ የተሰረቀ ሃሳብ መሆኑን ለማወቅ መረመረ፡፡ ደግሞ አስነበበ፡፡ ደግሞ መረመረ፡፡
እንደዛ አይነት ግጥም በእርግጥም ከእሱ ውስጥ ወጥቶ አያውቅም፡፡ መረጋጋት አቃተው፤ ግራ ተጋባ፡፡ ልክ እግዚአብሔር በመንበሩ ላይ ከእነ ሁሉን ቻይ፣ ሁሉን አዋቂ ማንነቱ ጋር ተረጋግቶ ባለበት ጽበት…መላዕክቶቹ ስለ ሌላ እሱ ሰምቶ ስለማያውቀው ሌላ ከእሱ በላይ ሃያል ስለሆነ አዲስ መጤ እግዚአብሔር የነገሩት መሰለው፡፡ ሊረዳ አልቻለም፡፡ ከእሱ ውጭ ሌላ እሱ ሊኖር አይችልም፡፡ ከእሱ ውጭ ሌላ (ወጣት) እሱ ከየት መጣ? መጽሐፉን ተቀብሎ አገላበጠ፡፡ ከማገላበጥ በኋላ አደብ ገዝቶ አነበበው፡፡ በእያንዳንዱ ገፅ…ይህ ያልታወቀ ገጣሚ ከኋላው ሲሮጥ እንደነበር እንኳን ሳያየው ድንገት ፈትለክ ብሎ የዘላለምን የፍፃሜ መስመር ከእሱ ቀድሞ ሲገባ ተመለከተ፡፡ የመጀመሪያው ገጽ ላይ ያለው ግጥም ከእሱ የመጨረሻ ግጥም ይበልጣል፡፡ የዚህ አዲስ ገጣሚ አንድ የመጀመሪያ መድበል የእሱን አምስት መድበሎች እንደ በግ ሲያግዳቸው በምናቡ ተሳለበት፡፡ የተሳለበትን ግን ግጥም አድርጐ የመፃፍ አንጀት አልነበረውም፡፡ ጽፎ መብለጥ ከሚችላቸው ከዘወትር መጠኖቹ ውጭ ነው፡፡ በአፉ መጽሐፉ እንደማይረባ ለመናገር ቢፈለግም ነሱፍ አልታዘዝ አለው፡፡ ነፍሱ የተሰጣትን እጣ ፈንታ መሸከም ሳትችል ለዝምታ አሳልፋ ገጣሚውን ስትሰጠው ያስተዋለበት ቅጽበት ይሄ ብቻ ነበር፡፡ የእሱን መጽሐፍት በግ አድርጐ የሚያግድ መጹሐፍ፣ ከፈጣሪ የመጣ ሊሆን እንደማይችል ለራሱ አስረዳ፡፡ “ይሄ አዲስ መጽሐፍ የተፃፈው በራሱ በሰይጣን እጅ ነው” ብሎ ለመጽናናት ድራፍት አዘዘ፡፡ ድራፍቱን እንደ ጭንቀት ማውራረጃ  ከዚህ ቀደም ተገልግሎበት አያውቅም፡፡ ግጥምን ለማዋለድ የሚያምጠው ምጥ እና ጭንቀት ለማስወገድ የሚማጥ ምጥ ለየቅል ናቸው፡፡ “አዳም ከገነት ሲባረር” በሚል ከዚህ ቀደም ጽፎት በአህዛቡም ተመስክሮለት የነበረውን ግጥም ምንም ስለፃፈው ነገር ሳይገባው መቀኘቱን ድንገት ተረዳው፡፡ አዳም ከገነት ሲባረር የተሰማው ስሜት፣ ገጣሚው ከተሰማው የመበለጥ ስሜት ጋር ብቻ ነው ሊወራረስ የሚችለው፡፡ አዳም ከገነት ሲባረር ባይተዋር ነው የሆነው። የፈጣሪ ልጅ የነበረ ሰው የፈጣሪ ጠላት ሆነ፡፡ በገነት ያሻውን በልቶ…ያሻውን ተኝቶ የሚያልም ሰው ወደ ምድር ሲጣል ሊሰማው የሚችለው ባይተዋርነት ብቻ ነው፡፡ የፈጣሪ ባለሟል የነበረው ገጣሚ ድንገት ብኩርናውን እንደተነጠቀ ገባው፡፡  
ይሄ አዲስ ገጣሚ ሰይጣን ነው ቢልም፣ ሰይጣን የጥበብ ፈጠራ መስራት እንደማይችል ያውቃል፡፡ ጥበብ የሚመጣው ከፈጣሪ ውክልና ብቻ ነው፡፡ ከገነት ተባርረው አዳም መሆኑ ድንገት ተገለጠለት፡፡ ፈጣሪ አዳምን የተካው በአንድያ ልጁ ክርስቶስ ነው፡፡ ከአራት ኪሎ ገነት ውስጥ ፈጣሪ አስቀምጦት አምስት የግጥም መድበል የሚሞሉ ስንኞችን ፃፈው በሌላ ከሱ በበለጠ ሊተካው ነበር ለካ፡፡ አዳም የዕጸ በለስ ፍሬዋን አትብላ ተብሎ የተሰጠውን ማስጠንቀቂያ በመተላለፉ ነው ከገነት የተባረረው፡፡ ገጣሚው ምን አጥፍቶ ከቀድሞ አማናዊ ዙፋኑ እንደተገፈተረ ሊገለጽለት አልቻለም፡፡ ሄዋን አይደለችም ያሳሳተችው፡፡ የሴት ዘርን ላለመቅረብ ሁልጊዜ ጥንቁቅ ነው፡፡ ጥንቁቅ አዳምን ሆኖ ነው የኖረው፡፡ ጥበብን ብቻ ከፈጣሪ ወደ ሰው ለማስተላለፍ ነፍሱን ጠብቆ፣ ስብን አቅልጦ ሳይመቸው የኖረ ነው፡፡ ታዲያ ፈጣሪ እሱኑ ባለሟል አድርጎ ለምን ሳያስቀጥለው ቀረ? ለምን ሌላ እረኛ በእሱ በጎች ላይ ሾመበት? ከዛ በኋላ ያሉት ቀናት እንደ ቀድሞው ሊሆኑለት አልቻሉም፡፡ እየተንጠባጠቡ በዙሪያው ይሰበሰቡ የነበሩት ወዳጆቹ… እየፈሰሱ ሟምተው ተሰወሩ። የተሰወሩት የት ነው? ብሎ ትንሽ ካጠያየቀ በኋላ የማይቀረውን እውነት ሰምቶ ጥርጣሬውን አረጋገጠ፡፡ በጎች ሁሌ እረኛ ይፈልጋሉ፡፡ ጠንካራው እረኛ የበለጠ በግ ይሰበስባል፡፡ ደካማው ደግሞ የበለጠ በግ መሰብሰብ አቅቶት ይበትናል፡፡ ደካማ መሆኑን መቀበል አቃተው፡፡ አባቱ ከፈጣሪ ተማክሮ ያወጣለት የእጣ ፈንታው ማህተም ተከተበበት ስም ሳይለው ትንቢቱ እንዴት እንደተለወጠ ሊገባው አልገባውም፡፡ የዘመን ጥርሶቹ እንዴት የሱን የብርሃን ስም አና የእጣ ፈንታውን ኮከብ … ልክ እንደ ወረቀት ቀዳዳው እንደጣሉ ማወቅ አልቻለም፡፡ እጣ ፈንታው እሱን ጥሎ ወደ ሌላ ሄዶበታል። መክሊቱ ተሰርቋ፤ በዚህ ወጣት፡፡ የወጣቱን ስም
መረመረው፡፡ ትዕቢት እንጂ የትንቢት ቅንጣት በውስጡ የማይተረጎም ስም ነው፡፡ የተጠየፈውን መፅሐፍ ገዝቶ በራሱ እልፍኝ በድብቅ መረመረው፡፡ በመረመረው ቁጥር እየገዘፈ ስለሚመጣ ምርምሩን ገታው፡፡ ምርምሩን ከቀጠለ የራሱን መጽሐፍ ለአዲሱ ገጣሚ እንደ እጅ መንሻ በማበርከት በግ መሆኑን የመግለጽ ፍላጎት እንደሚጠናወተው ታውቆታል፡፡ ወደ አራት ኪሎ መሄዱን አላቆመም፡፡ አድባሩ ሰፈር መቀየሯን ቢያውቅም ሊከተላት ካልቻለ … ድሮ ከትማ በነበረበት ተቀምጦ ስጋና ደሟ ሳይሆን ጥላዋን ቢያመልክ እና ቢማፀን ስለሚሻለው ነው፡፡ ቡና መጠጣት ባይፈልግም ቡና ግን ሱስ ሆኖ እንዲፈልጋት የማስገደድ ደረጃ ደርሳለች፡፡ ድራፍትም በእሱ ሳይሆን በእሷ ቁጥጥር ስር ስለመሆኑ ማረጋገጫዋን በብርጭቆ ብዛት ደርድራ አስቆጠራለች፡፡ ደከመው አዳምን፤ ደከመው፡፡ በብርታቱቲ ዘመን ተሰምቶት የማያውቀው የሴት አስፈላጊነት ለመጀመሪያ ጊዜ ተሰማው፡፡ ሄዋን ድሮ እንደሚያስባት እንዳልሆነች የታወቀው እንደ ድሮው ማሰብ ሲያቆም መሆኑ ደንቆታል፡፡ ሄዋን ድካምን አምጪ ነበረች በገጣሚነቱ ብርታት ዘመን፡፡ የእግዜር አንደኛ ምርጫ በሆነበት ዘመን፡፡ ከምርጫ ወደ ምርጫ ሲወርድ የሄዋንም ምንነት አዲስ ትርጉም ቀየረ፡፡ ሄዋን ለአዳም ገነት
በነበረበት ቆይታ የስህተት ምንጩ ነበረች፡፡ ከገነት ከተባረረ በኋላ ግን ሄዋን ለአዳም ድካሙን የምታበረታ ምርኩዙ ሆነች፡፡ ለካ በብርታቱ ዘመን በኤደን ገነት እግዜር አንፀባራቂ ነጭ መስታወት በነበረ ጊዜ ሄዋን ያላሳሳተችው አዳም ነበር ገጣሚው፡፡ ሄዋን ያላሳሳተችው አዳም ከገነት አይባረርም ማለት አይደለም ለካ፡፡ ለካ መባረሩ በጣም ወረደ አይቀርለትም፡፡ ለካ እጣ ፈንታው አዳምነት ነው። ለካ አዳምነት ከገነት መባረሩ ከኃጢያቱ ጋር ተያይዞ የተፈረደበት አይደለም፡፡ ከመጀመሪውም አዳም በመሆኑ የተፃፈለት እጣ ፈንታው እንጂ፡፡ ገጣሚው አዘነ፡፡ ደከመው፡፡ የሚያስለቅስ ግጥም ይጽፍ ነበር እንጂ ለካ በውን ከተወለደ ጀምሮ
አንድም ዘለላ እንባ አልቅሶ አያውቅም፡፡ አሁን አለቀሰ፡፡ ቀጣይ እጣ ፈንታው ከምሳሌያዊው አዳምም የከፋ መሆኑ ነው ያስለቀሰው፡፡ በገነት ሊኖር ተመኝቶ ከጎን አጥንቱ ያላሰራት ሄዋን ከተባረረ በኋላም ተከትላው አትመጣም ለካ፡፡ ድካሙን የምትደግፍ አፍቃሪ … ከገነት ከተባረረ በኋላ አልገኝ አለች፡፡ ግጥሙን ይወዱ የነበሩ ሴቶችም ገጣሚውን ለካ ወደው ያልቀረቡት በእጣ ፈንታው ምክንያት ነው፡፡ በድል አድራጊነቱ ዘመን አራት ኪሎ ያራቃቸው ሴች፣ በውድቀቱ አራት ኪሎ ላይ ሊደግፉት አልቻሉም። ከቡና፣ ድራፍት ከጂን የተረፈ ገንዘብ እያጠራቀመ ወደ ጨለማው ሰፈር አርቴፊሻል ሄዋን ፍለጋ መግባት ጀመረ። ከጊዜያት በኋላ አደስ የተመረጠው፣ ከእሱ የበለጠው እረኛ … በብዙ በጎቹ ተከቦ ወደ እሱ ካፌ መጣ፡፡ የመጣው ሊተዋወቀው እንደሆነ ነገረው፡፡ እሱ ባይዋጥለትም እንደሚያደንቀውም አረጋገጠለት፡፡ አኳኋኑ ሁሉ እንደክርስቶስ ሆነበት፡፡ በጣም ከፍ ያለ ሆኖ ሳለም ዝቅ ያሉትን ሁሉ ያከብራል፡፡ ከፍ ያሉ ስለመሆናቸውም ይነግራቸዋል፡፡ ለእሱም ነገረው፡፡ በእሱ አንደበት ሲነግረው ከቁጥጥሩ ውጭ አመነው፡፡ ድካሙን የሚያበረታ ንግግር ሰጠው “ያንተ አይነት ገጣሚ ስራ መቼም አይዘነጋም፡፡ ቢዘነጋ እንኳን ወደፊት ተመልሶ ገና መሆኑ አይቀርም” አለው አዲሱ እረኛ፡፡ እውነተኛው ገጣሚ፡፡ እውነተኛው ገጣሚ የተናገረውን የተስፋ ቃል፣ አዳም በምሳሌያዊ ጆሮው ነው ያደመጠው፡፡ ምሳሌያዊ ጆሮው የወጣቱን ገጣሚ ንግግር “ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ” ብሎ ነው የተረጎመለት፡፡ የልጅ ልጆቹ ታሪክ ሲያጠኑ… የሱን ግጥም እንደው አንዴ እንኳን አንስተው በትምህርት ቤት ውስጥ ከተማሩበት ትንቢቱ ተሳካ ማለት ነው፡፡ ሊድን የሚችለው እንደዛ ከሆነ ብቻ ነው፡፡ በተረፈ ግን እውነተኛ ገጣሚ ሲወለድ የሱንም ሞት እግረ መንገዱን አብስሯል፡፡ የአዳም ሀጢአት በክርስቶስ ትንሳኤ ፀድቷል፡፡   

Published in ልብ-ወለድ

የመጽሃፉ ርዕስ - የቄሳር እንባ
ደራሲው - ሃብታሙ አለባቸው
የገጽ ብዛት - 408
የታተመበት ጊዜ - 2007 ዓ.ም
የመጀመሪያው ስሜቴ
አስቀድሜ ያነበብኩት በመጽሃፉ የጀርባ ሽፋን ስለመጽሃፉ የተሰጡ አስተያየቶችን ነበር፡፡ አስተያየቶቹ ከአንዱ በስተቀር ደራሲው ከዚህኛው በፊት ላሳተሙት “አውሮራ” የተሰነኘ መጽሃፋቸው የተሰጡ አስተያየቶች ነበሩ፡፡ የአገላለጽ መንገድ ካልሆነ በቀር መጽሃፉ ባነሳው ታሪክ፣ በአጻጻፍ ዘዴው፣ በታሪኩ ፍሰት እኔም በእጅጉ ደስተኛ ነበርኩ፡፡ ፖለቲካ እና ፍቅር የአንድ ቤተሰብ አባል ሆነው በቀረቡበት “አውሮራ” መጽሃፍ ላይ የተፈጠሩ ገጸ ባሕሪያት፣ አንዳንድ ታሪኮች እንዲሁም የገጸባህሪያቱ ስያሜዎች በአብዛኞቹ በገሃዱ አለም የምናውቃቸው መሆን ይሕ መጽሃፍ ልቦለድ ነው? እውነተኛ ታሪክ? ወይስ ታሪክ ቀመስ ልቦለድ? የሚሉ ጥያቄዎችን አጭሮብኛል፡፡ ከዚህም ባለፈ ታሪክ ቀመስ ልቦለድ ቢባል በታሪኩ እና በልቦለዱ መካከል ያለው የእውነት ድንበር የቱ ነው? አንደኛው የአንደኛውን ድንበር ሲያቋርጥ የሚፈጠረውንስ ያለመረዳት እንዴት ማስታረቅ ይቻላል? የሚሉት ጥያቄዎች መልስ ያጣሁላቸው ተጨማሪ ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ ጥያቄዎቼ መልስ
እንዳጡ ይልጥ መልስ ሊያሳጡኝ ደራሲው አሁን ደግሞ “የቄሳርን እንባ” ይዘው መጡ፡፡የቄሳር እንባ እና ፍቅር
እንደ አውሮራ ሁሉ ይህም  መጽሃፍ በአጻጻፍ ቴክኒኩ፣ በፖለቲካዊ ትንታኔው እና በገጸ ባሕሪያት አሳሳል ድንቅ ሆኖ ቀርቧል፡፡ እንደ ቀደመው “አውሮራ” ሁሉ በዚህም መጽሃፍ ፍቅር ከፖለቲካ ጋር እወዳጅ ብሎ ቁም ስቅል ሲያይ እና አንባቢንም ሲያሳይ አንብበናል፡፡ በምናባችን አይተናል። ሐምራዊት በተገለጸችባቸው ውብ አረፍተ ነገሮች ብቻም ሳይሆን በዚህ ጊዜ ብዙም ለስምነት ሲውል በማንሰማው መጠሪያዋ በቀላሉ የማትረሳ ሆና ቀርባልናለች፡፡ ደራሲው የሐምራዊትን እና የአፍቃሪዋን መቶ አለቃ በላይነሕ ደሴን (እርሱ የፕሬዝዳንት መንግስቱ ባለቤት የእህት ልጅ እና የመረጃ ምንጫቸው ሆኖ ቀርቧል) መጨረሻውን ሳያሳየን የራሳችሁ ጉዳይ ቢለንም ምርጥ የፍቅር ታሪክን በማቅረብ ግን አልጨከነብንም፡፡ ሊያውም ኢትዮጵያ በምትመራበት ቤተመንግስት ቅጽር ግቢ የቀረበው ይሕ የድብቅ የፍቅር ታሪክ (ፍቅር ሲደበቅ ደስ ይላል መሰል) አንባቢን ከመጽሃፉ ጋር አጥብቆ ለመያዝ አቅሙ አለው፡፡ ፖለቲካዊ ይዘት ያለው ስነጽሑፍ ብዙም የማይስባቸው ሰዎች ስለሐምራዊት ሲሉ ብቻ የቄሳርን እንባ እልፍ እልፍ እያሉም ቢሆን ማንበባቸው የሚቀር
አይመስለኝም፡፡ደራሲው ደግ ነውአራት ኪሎ ቤተ መንግስት ይዞን ገባ፡፡ ሊቀ መንበር መንግስቱ ስለሚኖሩበት ቤት፣ ስለ ቤተ መንግስቱ ቅጽር ግቢ አጠቃላይ ስዕልም ሰጠን። ይበልጥ ደግ ሆነናም ፕሬዝዳንቱ እንደ ባል እና እንደ አባት ሆነው ሲኖሩ ሊያሳየን ባለቤታቸው ውባንቺን ካወቁበት ቀን አንስቶ ሶስቱን ልጆቻቸውን ትምሕርት፣ ትዕግስት እና አንድነትን ከነየባሕሪያቸው አስተዋወቀን፡፡ ስለአባትዋ ቪኦኤ እና የያኔው የወያኔ ራዲዮ በተናገሩ ቁጥር ልጃቸው ትምሕርት በር ዘግታ ስታዝን አሳየን፡፡ ማትሪክ ያመጣች ጊዜም ኮረኔል መንግስቱ አራት ኪሎ ዩኒቨርስቲ ይሻልሻል ወይስ ጥቁር አንበሳ እያሉ ሲያስመርጧት አስነበበን፡፡ በጥቅሉም ስለ ቤተሰባዊ ሕይወታቸው ቤተ መንግስት እና ቤታቸው አስገብቶ አሳየን፡፡ እኛን ስለሚመሩን ሰዎች ቤተሰባዊ ሕይወት ብዙ በማናውቅበት እና እንድናውቅም በማይፈቀድልን ሃገር ነዋሪ ነንና ነው የደራሲውን ይሄንን ተግባር በእርግጥ የእውነቱን ነው የጻፈውን እየጠየቅሁ? ደግ ነው ያልኩት፡፡ ሳንተዋወቅ መሪና ተመሪ መሆን ግን ያሳዝናል፡፡ኮረኔል መንግስቱ ውባንቺን በአራዳ ቋንቋ የጠበሱበት መንገድም ደስ ይላል፡፡ እግራቸው ለወታደርነት ሥራ ጎጃም የደረሰው ሰውየው፣ የእህል እገሃባቸውን ሊያስታግሱ በገቡበት አነስተኛ የገጠር ምግብ ቤት ነበር ውባንቺን ያገኙት፡፡ ርሃብ በጣፋጭ ጥብስ፣ መጠማትም በጥሩ ጠጅ ተሸነፉ፡፡ የሥጋ ፍላጎትን እየሞሉ ሳሉ ማደላደያውን ቡና ሊያፈሉ አይናፋርዋ ውባንቺ ከመንግስቱ ፊት በቀረቡ ጊዜ የልባቸውን ሙላት የሚሰጧቸውን የትዳር አጋር አገኙ፡፡ መቼም ግጥምጥሞሹ ሸጋ ነበር፡፡ በዚህ ሁሉ አስደሳች የታሪክ ጉዞ ግን ዘና ብዬ እያነበብኩ እኚህ ደራሲ የጻፉት እውነት ነውን? ስል እጠይቃለሁ፡፡ ከተጻፈው ሁሉ የትኛው ልቦለድ? የትኛውስ እውነት ነው ስል እጠይቃለሁ፡፡የኮሎኔሉ የሥልጣን ጉዞ
የጉዟቸው ማለፊያ እና ማረፊያ ሁሉ ሞት፣ አጃቢያቸው ደግሞ ግትርነትና የጦር መሳሪያ ሆኖ በስልጣናቸው የዘለቁት መንግስቱ፤ ከውስጥ ወደ ውጭ ማየት የማይችሉ ሆነው ቀርበዋል። ሁልጊዜም ራሱን ብቻ የሚያዳምጥ፣ እንወያይ ብሎ እንኳን ሰብስቦም ለሌሎች ሃሳብ ተግባራዊነት ጊዜ የማይሰጠው አምባገነንታቸው ሞትን ከቤተ መንግስት ቅጥር እስከ ጦር ሜዳ ሲጠራና ሲያመጣ የሥልጣን ዘመናቸው ያልቃል፡፡ የቅርብ ሰው ሆኖ ግደል ያሉትን ሁሉ ሲገድልና ሲያስገድል የነበረው አስር አለቃ፣ ኋላ መቶ አለቃ የሆነው ምስጋናው በማዕረግ እድገቱ የደስ ደስ የግድያ ጀብዱውን ሲያወራ በልጃቸው መሰማቱ እርሳቸውም ጆሮ ደርሶ እንዲገደል መደረጉ አንባቢን ያስደነግጣል፡፡ ግን ይሄስ ነገር እውነት ነውን? ስል እጠይቃለሁ፡፡የሚሰወድባቸውን አብዮታዊ እርምጃ አንደግፍም ለምን በጡረታ አይሰናበቱም? የሚል የውሳኔ ሃሳብ እየቀረበላቸው ውሳኔውን ወደ ጎን አድርገው በጄነራሎቻቸው ላይ ሞትን ሲፈርዱና ሲያስፈጽሙ የኖሩት መንግስቱ፤ በቅጡ አልገባቸውም በተባሉበት የሶሻሊዝም ርዕዮተ አለም ሲዳክሩ እንደኖሩ የጻፈልን ደራሲ፤ መንቃታቸውን እና የመጨረሻ  ዕንባቸውን እየናፈቀ በልግመተ ኢትዮጵያ ሃሳቡ መቶ አለቃ በላይነህን ተራኪ አድርጎ ያስነብበናል፡፡ የታሪኩ ዋና ማጠንጠኛ የሆኑት ፕሬዝዳንት መንግስቱ እና ባለስልጣኖቻቸው  (እያንዳንዳቸው ከነእውቀት እና ባሕሪያቸው በመጽሃፉ ቀርበዋል፡፡) ኢትዮጵያን የመሩበትን የጦር መንገድ፣ ሶማሊያን ድል የመቱበት ብርታት፣ ያለፍንባቸውን የድርቅና የእርስ በእርስ ጦርነትን ጊዜ በቄሳር እንባ ላነበበ የዛሬ ትውልድ እንኳንም ያንን ጊዜ አልኖርኩበት ብሎ ቀድሞ መመኘቱ የሚቀር አይመስለኝም፡፡እባክዎ ደራሲው ይንገሩኝ
በመጽሃፉ ላይ አብዛኞቹ የተሳሉት ገጸ ባህሪያት በገሃድ አለም የሚታወቁ ናቸው፡፡ በመቶ አለቃ በላይነህ ደሴ ሲቀርብ የነበረው የፖለቲካ ትንተናም ንድፈ ሃሳባዊ ብቻም ሳይሆን በተግባራዊ እውቀት የተደገፈ ስለመሆኑ በግልጽ ይታያል፡፡ ገጸ ባህሪያቱን ከፖለቲካ ትንታኔው ጋር ላዋደደ ሰው የሚያነበው ሁሌ እውነት ነው ብሎ ለማመን የሚገደድ ይመስለኛል፡፡ እኔ እንደዚያ ተሰምቶኛል፡፡ ከስሜት ባለፈ ግን እውነ ትመሆኑን ለማረጋገጥ ደራሲው ይሄንኑ በመጽሃፉ በመግለጽ እውነቱን እንድናውቅ እድሉን አልሰጡንም፡፡ በመጽሃፉ የተገለጹ ድርጊቶችን እና ቁጥሮችን ለሌላ ስራ በማጣቀሻነት ለማቅረብ የሚፈልግ አንባቢም ሆነ የታሪክ ባለሙያ በዚህ ረገድ የሚቸገር ይመስለኛል፡፡ ደጋግሜ እንዳነሳሁት አቶ ሃብታሙ መጽሃፉን ድንቅ አድርገው አቅርበውታል፡፡ በዚህ ላይ ጥያቄ የለኝም፡፡ ምርጥ መጽሃፍ ነው፡፡ ጥያቄዬ መጽሃፍዎት እውነተኛ ታሪክ ነው ወይስ ልቦለድ? ምን ያህሉስ እውነት ነው? የሚለው ነው፡፡ ጥያቄዬ መጽሃፍዎት እውነት እና ልቦለድን
አጋብቶ ያቀረበም ከሆነ እንደ እኔ ያለ አንባቢዎ ይሄንን ለመለየት ድንበሩን ለማወቅ አይቸገርምን? የሚል ነው፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን ሌሎች ሥራዎችዎንም ለማየት ከሁሉም የሚበልጠው የአዕምሮ ሰላም ከእርስዎ ጋር
እንዲሆን ከልቤ እመኝልዎታለሁ፡፡

Published in ጥበብ
Page 11 of 19