Saturday, 02 May 2015 11:46

የፍቅር ጥግ

ሚስት በባሏ ላይ ከመንግስት የበለጠ ሥልጣን አላት፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኤመርሰን
ሰው ሚስትህን ሲሰርቅብህ እንዲወስዳት ከመፍቀድ የበለጠ በቀል የለም፡፡
ሳቻ ጉይትሪ
ሚስትህን ፈፅሞ አትምታት - በአበባም ቢሆን፡፡
የሂንዱ አባባል
ሚስቴ አለቀሰች፡፡ ዳኛው በእኔ “ቼክ” እንባዋን አበሱላት፡፡
ቶሚ ማንቪሌ
ወንደላጤዎች ከባለትዳር ወንዶች የበለጠ ስለ ሴቶች ያውቃሉ፡፡ እንዲያ ባይሆን ኖሮ እነሱም ያገቡ ነበር፡፡
ኤች.ኤል.ሜንኬን
ባሎች እንደ እሳት ናቸው፤ ካልቆሰቆሷቸው ይጠፋሉ፡፡
Zsa Zsa Gaber
ሚስት የሌለው ወንድ፣ አበባ የሌለው የአበባ ማስቀመጫ ማለት ነው፡፡
የአፍሪካውያን አባባል
ማንኛውም ያገባ ወንድ ስህተቶቹን መርሳት ይኖርበታል፡፡ ሁለት ሰዎች ተመሳሳይ ነገር ማስታወሳቸው ጥቅም የለውም፡፡
ዱአኔ ዴዌል
ስለ ፍቅርና ስለ ትዳር ማንበብ ከፈለግህ ሁለት የተለያዩ መፃህፍት መግዛት አለብህ፡፡
አላን ኪንግ
ከልብ የወጣ ልብ ይነካል፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
ፍቅር፤ ምንም ነገር የመጋፈጥ ኃይል ይሰጠኛል፡፡
አሊሰን አስርንዎልፍ

Published in ጥበብ
Saturday, 02 May 2015 11:45

የግጥም ጥግ

አ ቤት!
ኤሎሄ  ቅኝቱ  ጠፍቶኝ
የነገለ በገና አቅፌ
በጉልበቴ ተቀምጬ፤
በፍታቴ እስክስታ ብወርድ
እዝል አራራዩን ባላዝነው
ቅኔ ማህሌቱን  ገልብጬ፤
የሀሩር በረሀ አበባው
ዋግ እንዳጠናፈረው እሸት
እማሳው መሀል ብገተር፤
አለቅጥ ጠግበው በሚያናፉ
ዝሆኖች መሀል እንደ ድርጭት
አቅሌን ስቼ እምውተረተር፤
ፈተና ያቆመኝ ሀውልት
አልሟሟም ያልኩ ቢመስል
ባያነባ ሙጭሙጭ አይኔ፤
እምነቴ ቢያጠጥረኝ ነው
ምናቤ የረገጠው እርካብ
ቢያዝለኝ ጣራ ውጥኔ፡፡
እንደ ምኞታችንማ ጉስቁልና
እንደ ሚዛናችን መራቆት
እንደ ነፍሳችን ግልቢያ መጃጀት፤
መርዷችን ባይሰማ እንጂ
ወገን ከሌለንማ ቆየን
እንደ ሩቁ ተስፋችን መዘግየት፡፡
አቤት!    አቤት!!    አቤት!!!
/ፈለቀ አበበ፤ 1989 ዓ.ም -
ተረት ሰፈር/

Published in የግጥም ጥግ
Saturday, 02 May 2015 11:41

ዓይናፋሯ የሎግያ ከተማ!

የሌላ አገርን ዝናብ ዳመና፣ ጉምና ጭጋግ ያጅበዋል፡፡ የሎግያ ሰመራን ዝናብ ደግሞ  እንደቤተ-ዘመድ አቧራ ያጅበዋል፡፡ ዝናብም በሰማይ ያገኘውን አቧራ እየጠረገ  ከሰማይ ወደ መሬት ሲወረወር፣ የዝናብ ትርዒት ወይም ውድድር የምታይ ይመስልሃል፡፡ አንተ የምታውቀው ከዝናብ ጋር የሚወርድ በረዶ ከሆነ በዚህ ግን  ፌስታል፣  ፕላስቲክ፣ ካርቶን፣ የጫት ገረባ፣….የመሳሰሉትን ናቸው፡፡

  ‹‹የበርሀ ውሃ የቀመሰ ሌላ አገር ሄዶ አይለምድም››  ሲባል ሰምተህ ይሆናል፡፡ ተረት ተረት እንዳይመስልህ፡፡ ሞክረህ ማረጋገጥ ትችላለህ፡፡ ማንኛውም ተራ ተርታ ሰውና ከፍተኛ ባለስልጣናት ያለ ልዩነት እኩል የሚኖሩባት ሥፍራ ያለው በእዚህ በዓይናፋሯ ከተማ ሎግያ ውስጥ  ነው፡፡
በበርሀ የሚኖሩ ማህበረሰቦች ለሚበላና ለሚጠጣ ነገር አይጨካከኑም፡፡ ተደብቆ መብላትን፣ እያለው የለኝም ማለትን ነዋሪዎቹ አያውቁበትም። መተጋገዝ፣ መተሳሰብ ሰብአዊነት ብቻ ሳይሆን የውዴታም ግዴታ ነው፡፡ ለብቻህ ለየት ማለት ብትፈልግም የበርሀው አየር በራሱ አይፈቅድልህም። ስስታሙን ቸር፣ ጨካኙን ሩህሩህ፣ ዝምተኛውን ተጫዋች በማድረግ  ረገድ የበርሀ ውሃ  ትልቅ ተጽእኖ አለው፡፡ በዚህች ከተማ ባይኖርህም አትራብም፣ አትጠማም፤ ቢኖርህም ከማንም አትበልጥም፤ መንቀባረርም አያምርብህም፡፡
በድሃና በሀብታም መካከል ያለው ልዩነት አንዳንዴ ከስም የዘለለ የማይሆንበት ጊዜ አለ። የሰው ልጅ የሚከበረው በሰውነቱ እንጂ ባለው የገንዘብ መጠን አይደለም ይሉሃል፡፡ አንቱታ ከፈለክ ሲያምርህ ይቀራል እንጂ የሚያጎበድድልህ አይኖርም፡፡ ለምሳሌ በርሀ የተወለደ ልጅ ‹‹የአባዋራ አልጋ ላይ አትቀመጥ›› ቢሉት መደናገር ብቻ ሳይሆን ግርምትም ይፈጥርበታል፡፡ ምክንያቱም በዚህ አካባቢ ከአልጋ  ይልቅ ጋሌታ ታላቅ ክብር አለው። ደግሞ ይሄ የኔ ነው፤ ያ ያንተ ነው የሚል ገደብና አጥር በዚህ አካባቢ አይታወቁም፡፡ ቀለል አድርጎ ቀለል ብሎ መኖር ነው እንጂ፡፡
ሙቀቱን ፈርተው  ሥራ የቀየሩ ወይም የለቀቁ ወራት ሳይቆዩ በናፍቆትና በአካባቢው የኑሮ ፍቅር ተነድፈው ብዙም ሳይቆዩ ይመለሳሉ፡፡ ያኔም ‹‹የበርሀ ውሃ የቀመሰ ሌላ ቦታ ሄዶ አይለምድም›› ብለው በፍቅር ይቀበሉሃል፤ ጎረቤቶችህ እንደበፊቱ ይንከባከቡሃል፡፡ መደገፍም ካለብህ ያቋቁሙሃል፡፡
ከተለያዩ የፌደራል መስሪያ ቤቶች ተልከው የመጡ  ኦዲተሮችና አማካሪዎች  ሳይቀሩ እዚሁ ሰምጠው ቀርተዋል፡፡ ምክንያቱም ኑሮን ቀለል አድርጎ የሚኖር፣ የማያካብድና ፍቅርን የማይነፍግ ማህበረሰብ በዚህ አለ፡፡
የማወራችሁ የአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት መዲና ስለሆነችው ሰመራ ሎግያ ከተማ ነው፡፡
በአይናፈሯ ከተማ ሎግያ ሠመራ፤ ብዙ አስገራሚና አስደሳች ነገሮች በየዕለቱ ይስተወላሉ፡፡ ለምሳሌ የዝናብ ሠርገኛ በየትም ሀገር የሚታወቀው ጥቁር ደመና አለዚያም ጭጋግና ጉም ነው፡፡ ነገር ግን በሎግያ ኑሮ ብቻ ሳይሆን፣ ሙቀት ብቻ ሳይሆን፣ ፍቅር ብቻ ሳይሆን፣ ንግድ ብቻ ሳይሆን፣ አኗኗር ብቻ ሳይሆን የዝናብም አመጣጥ የተለየ ነው፡፡
 ከምስራቅ የሰማዩን ጥግ ይዞ ሲገሰግሰስ የምታየው ግጥም ያለ ጥቁር የደመና ደለል  ሊመስልህ ይችላል፡፡ ሲቀርብህ ግን ጠራርጎ የሚወስድህ ነፋስ ሆኖ ታገኘዋለህ፡፡ የገርጀሌ ሜዳን አቧራ ተሸክሞ አምጥቶ ያለ ወዛደር ያራግፍብሀል፡፡ አንተ ያኔ አቧራህን በፍጥነት ካላራገፍክ እሱን አጅቦት የሚዘንበው ዝናብ ወይ ያጥብሀል አለበለዚያም ጭቃ ላይ የተንደፋደፍክ ያስመስልሀል፡፡  
የሌላ አገርን ዝናብ ዳመና፣ ጉምና ጭጋግ ያጅበዋል፡፡ የሎግያ ሰመራን ዝናብ ደግሞ  እንደቤተ-ዘመድ አቧራ ያጅበዋል፡፡ ዝናብም በሰማይ ያገኘውን አቧራ እየጠረገ  ከሰማይ ወደ መሬት ሲወረወር፣ የዝናብ ትርዒት ወይም ውድድር የምታይ ይመስልሃል፡፡ አንተ የምታውቀው ከዝናብ ጋር የሚወርድ በረዶ ከሆነ በዚህ ግን  ፌስታል፣  ፕላስቲክ፣ ካርቶን፣ የጫት ገረባ፣….የመሳሰሉትን ናቸው፡፡
ያለምንም የዝናም  ጠብታ፣ የመብረቅ ጩኸት እና ብልጭታ የሰማዩን ጥግ እየቀረደደው ሲወርድ ስታይ ፎቶ የማንሳት ፍቅር  ካለህ ድንቅ ነገር ነው። አንሳው፤ ለፌዝ ቡክህ ይሆንሃል፡፡ እርግጠኛ ነኝ በአቧራ የታጀበ ድፍርስ ዝናብ የሚዘንበው በዚያ አካባቢ ብቻ ነው፡፡ እንግዲህ ለበርሀ ዝናብ የውሃ ትነት ብቻ ሳይሆን የአቧራ ቡነትም ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡
ሌላው አስገራሚ ነገር  እየዘነበም ማቃጠሉን የማይተወው የቤት ሙቀት፣ የቦነነብህን አቧራ (በላብ) በፍጥነት ወደ ጭቃነት ይቀይረዋል፡፡
ዝናብ ሲዘንብ ሌላው አጃቢ መብራት ኃይል ነው፡፡ የመብራት ቦሎች (ባሎዎች) በንፋሱ ሃይል ሊወድቁ ስለሚችሉ አቧራው እንደተነሳ መብራት ወዲያው ይጠፋል፡፡ ያኔ በዝናብ ውስጥ የማይታመን ሙቀት ያቀልጥሃል፡፡  
አቧራ ሲመጣ ሁሌም መብራት ስለሚጠፋ የፋን ቅዝቃዜ እንኳን ለመጽናኛ አታገኝም፡፡ የመብራት ኃይል አጃቢ ደግሞ ቴሌኮሙኒኬሽን ነው፡፡ እንግዲህ የዝናብ አጃቢዎች ሁለት ታላላቅ መስሪያ ቤቶች፣ ብዙ ቆሻሻዎች ፣የምጻት ቀን ደረሰ እንዴ የሚያስብል አቧራ ናቸው፡፡
አልደብቅህም፤ ሙሉ ቀን ስታጥብና የቤት እቃዎቿን ስታስተካክል የዋለች ሴት መነጫነጭ የምትጀምረው ገና ነፋሱን በሩቅ ስታየው ነው። የተፈጥሮን ህግ ለማድነቅ ከሚያስገድዱ ነገሮች አንዱ በቀን ብዙ ጊዜ ቢነፍስም፣ ቀኑንም ሙሉ በአቧራ ብትውልም በዚህ ምክንያት እንኳን ሌላ በሽታ ጉንፋንም አይዝህ፡፡ አቧራ በሽታ ነው የሚልህ ሰው አታገኝም፡፡ ዶክተር ብታማክርም በዚህ አካባቢ በአቧራ ምክንያት የሚመጣ ችግር የለም፡፡ አቧራውም ይቦናል፤ ኑሮም ይቀጥላል፡፡
‹‹እንዴት በአቧራ ምክንያት ጉንፋንም አይዝህ ብለህ ታካብዳለህ›› ብትለኝ አልቀየምህም፡፡ ብዙ መልስ የሌላቸው ነገሮች በዚህ አካባቢ ታገኛለህ። ለምሳሌ በምትኖርበት ሰፈር በወር አርባ፣ ሃምሳ ህጻናት ሊወለዱ ይችላሉ፡፡ ለቅሶ ግን በወር አንዴም ላትሰማ ትችላለህ፡፡ ‹‹ሞት ተጠርዞ ከዚህ ተባሯል እንዴ?›› ያስብላል፡፡ አናትህን የሚበረቅስ ጸሃይ እየወጣ ፊትህን አይለበልብህም ወይም አያቃጥልህም፡፡ ቀዝቃዛ አካባቢ የሚኖሩ ሰዎች በጥላ ሲከለሉ ለይስሙላ እንኳን በኛ ምድር ጥላ አንጠልጣይ አታገኝም፡፡ ከማህጸን የወጣን ልጅ እንኳ የማይጋጭ የአየር ንብረት በዚህ አለ፡፡ ታድያ ምን እንላለን፡፡ ተፈጥሮ ግሩም ነው ብሎ ማለፍ እንጂ፡፡ ብዙ ተዓምር ቀስ እያልኩ አወራሃለሁ። በአምላክ ጥበብ እጅህን አፍህ ላይ ጭነህ እንድትገረም ካሰኘህ፡፡
የሎጊያ ከተማ  ሁሌም ቅዳሜ ምሽት የበዓል ዋዜማዋ ነው፡፡ ከተማዋ ቀንና ማታ ፍጹም ትለያያለች፡፡ ቀን ‹‹አንገት ደፊ አገር አጥፊ›› እንደሚባለው እንደ ልጃገረድ ስትሽኮረመም ትውልና ፀሀይ ለጽልመቱ ስፍራውን ሳታስረክብ ገና በቅጽበት  ሐፍረቷን ትጥላለች፡፡  ለዚህም ነው ዓይናፋሯ ከተማ ያልኳት፡፡
ቀን ራቁታቸውን በየበረንዳው ጫት ከሚሸጡትና ከሚያደቁት፣ እየተሯሯጡ በሀሩሩ ጸኃይ ከሚደልሉት፣ እንደ ወፍ ብር ብር ከሚሉት ባጃጆች፣ መንገድ እየዘጉ ከሚያስቸግሩት ከባድ መኪኖች በተጨማሪ አስፓልቱን ሞልተው የምታገኛቸው ተማሪዎችንና ትራፊኮችን ነው፡፡
ሠመራ ሎግያ ከቅርብ ዓመታት ጀምሮ ታላቅ ለውጥ በማምጣት ላይ ትገኛለች፡፡ ይህ ሪፖርት እንዳይመስልህ፡፡ ከዛሬ አምስት እና አስር ዓመታት በፊት እንግዳ ቢመጣ የሚያርፍበት ሆቴል እንኳን ይቸግር ነበር፡፡ አሁን ግን ማማረጥ ትችላለህ። ሎግያ ብትፈልግ ካሰኘህ ሠመራ በኤሲ ቅዝቃዜ የተንበሻበሹ ሆቴሎች ተገንብተዋል፡፡ እሰይ የሚያስብልን ነገር እሰይ ማለት ይበጃል ብዬ ነው። ለነገሩ በቀደሙት ዓመታትም ቢሆን ሎግያ ሠመራ ከተማ ለማደግ ሳትመች ቀርታ እንዳይመስልህ፡፡  በሎግያ ከተማ ተሸቅሎ በሌሎች ከተሞች ስንትና ስንት ፎቅ እንደተሰራ አዳማ፣ አዲስ አበባ፣ መቐሌ፣ ኮምቦልቻ እና ደሴ ምስክሮች ናቸው፡፡
ያም ሆነ ይህ ምንም እንኳን ጥናት ባላደርግም አሁን ያለችበት እድገት ጥሩ ይመስላል፡፡ በከተማዋ ውስጥ ያሉ ነዋሪዎች፣ ነጋዴዎች፣ መንግስት እና ግለሰቦች ለልማቱ መፋጠንም ሆነ መጓተት መንስኤ ናቸው፡፡
ንግድ በሎግያ ከተማ በከራማ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ እቃ ልትገዛ ሄደህ የመቶ ብሩን ሁለት መቶ ሃምሳ ይሉሀል፡፡ ሌላ ከተማ ሄደህ ብትገዛ ብዙ ወጪ እንዳለብህ ስለምታውቅ አማራጭ አይኖርህም፡፡ ወይም ዋጋው ይሄ ይመስልሀል፡፡  በሁለተኛው ቀን  ልትገዛ ከተመልስክ  ወዶታል ማለት ነው በሚል እሳቤ  “ሶስት መቶ” ልትባል ትችላለህ፡፡ “ትላንት  ሁለት መቶ ሸጠህልኝ?!” ካልከው  ‹‹አመጣጡ ነው›› ብሎህ ያርፋል፡፡ “ባንዴ መቶ ብር ታድያ እንዴት ይጨምራል?” ስትለው ደግሞ፤ ‹‹ትናንት በገዛሃ›› ይልሀል፡፡ አለበለዚያም ‹‹ወላሂ፣ ነብያችንን፣ እመብርሃንን፣ መድሃኒያለምን ፣ ገብርኤልን” በማለት አዲስ እንደመጣ ሊያስረዳህ ይኳትናል፡፡
አንዳንዱ ደግሞ  እንደ አመለኛ በሬ ‹‹እፍ..›› በማለት አፍንጫውን ነፍቶ፣ በንቀት አይቶህ የማይከራከሩትን ያስተናግዳል፡፡ እያካበድኩ ከመሰለህ በዚች ከተማ የመርፌ ዋጋ እንኳን አንድ ብር ከአስር ሳንቲም ገብቷል፡፡ ያንንም ካገኘህ ነው፡፡ ደግመህ ከጠየቀከው ዋጋው እንደሚጨምር አትጠራጠር፡፡
አንዳንዴ ደግሞ ጥሩ ትርኢት ታያለህ፡፡ አንተ ላይ የተዘባነነብህን ባለሱቅ አንዱ አፋር መጥቶ፤ ‹‹አንተ አውቶቡስ በራው (መኪና የወለደህ)›› ሲለው አንጀትህ ቅቤ ይጠጣል፡፡ “መጤ” የሚለውን ቃል አውቶቡስ በራው የሚለው ይወከለዋል። ስለ መጤ ብዙ መናገር ይቻላል፡፡ አንተ መጤ ሲባል የምታውቀው ከሌላ ቦታ መጥቶ የሠፈረን ሰው ሊሆን ይችላል፡፡ ከሌላ ቦታ መጥቶ የሰፈረ አፋር “አውቶቡስ በራው” ይባል ይሆን? ኧረ ምን አደከመን፤ ወደ ዋናው ወሬያችን እንመለስ፡፡
 ሙዝና ቲማቲም ልትገዛ ሄደህ፣ ሌላ ሀገር የዘበኛ የወር ደመወዝ የሚያክል ጭማሪ ሊደረግብህ ይችላል፡፡ ምናልባት ‹‹እዚሁ ዱብቲ ከተማ በርካሽ እየተሸጠ›› ብትለው፤ ‹‹ታድያ ለምን እዚያ ሄደህ አትገዛም›› ይልህና ዘወር ብሎ ሌሎቹን ደንበኞች ያስተናግዳል፡፡ የተጠየቁትን ሳይከራከሩ የሚከፍሉ ብዙ ሰዎች ይገጥሙሀል፡፡ አንተ ብቻ ቀብቃባ እንደሆንክ ይሰማህና ሳትከራከር ትገዛለህ፡፡ ነገር ግን አንተ  በወር ደመወዝህ ብቻ  የምትኖር ከሆነ፣ በወሩ አስራ አራተኛው ቀን ላይ ብድር መግባትህ አይቀሬ ነው፡፡ ምክንያቱም አንተ የምትጋፋው ብር ከሚያፍሱ ሰዎች ጋር ሊሆን ይችላል፡፡
የቀን አይናፏሯን፣ የሌሊት መንጃጋዋን ሎግያ ከተማ ብር የሚያፍሱም የሚያፈሱም ሰዎች ይኖሩባታል፡፡ በከተማዋ የምትፈልገው ነገር ሁሉ አለ፡፡ ዋጋው ተራራ ቢያክልም እንኳ የሌለው ነገር የሌለ ብቻ  ነው፡፡
የማልደብቃችሁ ነገር በሎግያ ከተማ የማይገኙት የሸበተ ሽማግሌ  እና ባልቴት ናቸው። ምናልባት ሚስትህ አርግዛ ‹‹በምርኩዝ የሚሄድ ሽማግሌ ማየት  አማረኝ›› ብትልህ ጉድህ ይፈላል። ይህ ከሚያምራት አውሮፕላን ግዛልኝ ብትልህ ይሻልሃል፡፡
ሌላው ላታገኝ ትችላለህ ብዬ የምገምተው የፈለግኸው ዓይነት የሚከራይ ቤት ነው፡፡ የቤት አከራዮች ዋጋ እና ቤቱ ካለመመጣጠናቸው የተነሳ ዘጠኝ መቶ ብር የተባልከው ቤት ውስጥ  የተቀመጠ ስድስት መቶ ብር ያለ ሊመስልህ ትችላለህ፡፡
ሲጥጥ ሲጥጥ ሲል የጦር አውሮፕላን የሚመስል ፋን ገጥመው ‹‹ፋን አለው ፣መብራት አለው፣ ውሃ ግን ገዝተህ መጠቀም ትችላለህ›› ሲሉህ ላፋቸው እንኳን አይከብዳቸውም፡፡
እስኪ ልየው ስትል፤ ‹‹ቆይ ቆይ ብቻህን ነህ? ጓደኛ ታበዛለህ እንዴ? ስራህ ምንድን ነው?፣ ፍሪጅ አለህ? ስቶቭ ትጠቀማለህ?” የመሳሰሉትን ኢንተርቪው ካለፍክ በኋላ አፓርታማ እንደሚያከራይ ሰው እየተዘባነኑ ያሳዩሀል፡፡ አሪፍ ቤት ያገኘህ መስሎህ ስትገባ፣ የቤቱ ግድግዳ ከመጣመሙ የተነሳ የማርንጌጃ ዳንሰኛ የሚመስል ሊሆን ይችላል። አለዚያም  የግድዳው ቀለም ከማስጠላቱ ወይም ከማርጀቱ የተነሳ  የቀለማት ማህበርተኞችም እንደማያውቁት ትገምታለህ፡፡ ኮርኒሱ የአቧራ ማቆር ልማት  ላይ ሊመስልህ ይችል ይሆናል፡፡ በመደነቅ እጅህን አፍህ ላይ ጭነህ፤ ‹‹ይሄው ነው ዋጋው?›› ካልካቸው፣ ‹‹ብቻህን ስለሆንክ እንጂ ይጨምር ነበር›› ይሉሃል ኮራ ብለው፡፡
በአንተ ብር ቤተሰባቸውን ማስተዳደር እንዳማራቸው ወይም ሌላ አገር ያስጀመሩትን ቤት ለማስጨረስ እንዳሰቡ ልትገምት ትችላለህ፡፡ ግምትህ ስህተት ነው ብለህ አታስብ፡፡  ቤት በመፈለግ ደክሞህ ከሆነ ‹‹እሺ በቃ ለጊዜው ልከራየው›› ስትል፤ ‹‹ሴት ይዞ መምጣት ክልክል ነው›› የሚል ሌላ አንቀጽ ይጨምሩብሃል፡፡ ፍቅረኛው ልታየው መጥታ ሆቴል ተከራይቶ የሸኘ ወጣት እንደማውቅ እነግርሃለሁ፡፡  ግን ብዙ አትፍራ፡፡
እድለኛ ከሆንክ አሪፍ አከራይ ይገጥምህ ይሆናል፡፡ እናት የሆኑ፣ በዓመትህም ኪራዩን ብትከፍላቸው የማይቀየሙ አከራይዎችም በዚህቹ ሎግያ ከተማ አሉ፡፡  አንዳንድ ምርጥ ቤቶች ምርጥ ባለቤቶችም እንዳሉ ልጠቁምህ እወዳለሁ። አንተን ከነጉድህ መሸከማቸው ብቻ ሳይሆን ልጄ ብለው የሚጠሩህ አከራዪችም አሉ፡፡ ሲርብህ አጉርሰው፣ ሲጠማህ አጠጥተው አንቀባረው አኑረውህ፣ እዳህን ሳትከፍል ላሽ እንዳትል  ብቻ ተጠንቀቅ፡፡  ቀላቢት (የጫረው) በልተው የሚጠፉ ብዙዎች ናቸው፡፡ ምንም ሁን ግን ለአምላካቸው ብለው የሚወዱህ፣ ደግነታቸው በአደባባይ የሚመሰክርላቸው ሞልተዋል፡፡ “ተመስገን ነው” የሚል መጽናኛ  በምድር ላይ አለመጥፋቱ አትልም!
በነገራችን ላይ የቤት አከራዮች ባለትዳር ብትሆን ደስ ይላቸዋል፡፡ የቤት ሰራተኞች ደግሞ ወንደላጤ ስትሆን ይመርጡሃል፡፡ አከራዮች ባለትዳር የሚፈልጉት ግቢያቸውን ለማስከበር እንዲመቻቸው ሲሆን የቤት ሰራተኞች ደግሞ ወንደላጤ የሚወዱት ከአስዝቤዛ ከሚገኙ ትርፋ ትርፎች በተጨማሪ ከተመቻቹ ወደ ገደለው ጭልጥ ለማለት ነው ይባላል፡፡
በተከራይነት ገብተው ቤት የሰሩ እንዳሉ ሁሉ በሰራተኝነት ገብተው አግብተው፣ ወልደው የሚኖሩ የቤት ሰራተኞች በሎግያ በጣም ብዙ ናቸው፡፡ እንደውም አንዳንዶቹ  ፍቅረኛ ያለውን አስከድተው፣ ትዳር ያለውን አስፈትተው፣ ኑሮአቸውን በቁጥጥር ሥር ያዋሉ ናቸው ይባላል፡፡
(ይቀጥላል)

Published in ህብረተሰብ

ሠማያዊ ፓርቲ የአይኤስን የሽብር ድርጊት ለማውገዝ መንግስት የጠራውን ሠልፍ አውኳል በሚል በመንግስት እየተወነጀለ ሲሆን ፓርቲው በበኩሉ፤ በተፈጠረው ረብሻ እጄ የለበትም፤ መንግስት ያለ አግባብ የስም ማጥፋትና ውንጀላ ዘመቻ ከፍቶብኛል ሲል አማሯል፡፡ መንግስትና የመንግስት ሚዲያዎችን ጨምሮ የተለያዩ የመንግስት አካላት በፓርቲው ላይ የሚሠነዝሩትን ውንጀላ ካላቆሙም ፓርቲው ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት ሊወስደው እንደሚችል አስታውቋል፡፡ መንግስት ግን ሠማያዊ ፓርቲ ሁከቱን ስለመፍጠሩ በቂ ማስረጃ አለኝ ብሏል፡፡ በሌላ በኩል፤ ሠማያዊ ፓርቲ ሠሞኑን በቅስቀሳ ፖስተር አለጣጠፍ ጉዳይ ከብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ማስጠንቀቂያ ደርሶታል፡፡ በእነዚህ አወዛጋቢ ጉዳዮች ዙሪያ የፓርቲው የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ዮናታን ተስፋዬን የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ አነጋግሯቸዋል፡፡


ሠማያዊ ፓርቲ መንግስትንና የመንግስት ሚዲያዎችን እከሣለሁ ሲል ምን ማለቱ ነው?
መንግስት የፓርቲው ተግባር ያልሆነን ጉዳይ አንስቶ “በረቡዕ እለቱ ሠላማዊ ሠልፍ ላይ ሁከት የፈጠረው ሠማያዊ ፓርቲ ነው” በሚል በሃሰት መወንጀሉና በፍርድ ቤት ሣይረጋገጥ ጥፋተኛ አድርጐ በመፈረጁ፤ ፌደራል ፖሊስ “7 የሰማያዊ አመራሮችን አስሬያለሁ” ያለውም ሃሰት ነው፤ የታሠሩት 6 ናቸው፤ እነሱም ከሠልፉ በፊት ነበር የታሠሩት፤ አንደኛው የዚያኑ ቀን ነው የተፈቱት፡፡
ኢቢሲንም እንከሣለን ብላችኋል፤ ምክንያቱ ምንድን ነው?
የውሸት ዘገባ በማሠራጨቱ ነው፡፡ “አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪዎች” እያለ በምርመራ ያልተያዘን ጉዳይ አንስቶ ሠማያዊ ነው ሁከቱን ያቀነባበረው የሚሉ መሠረት የሌላቸው ስም አጥፊ ዘገባዎችን ሲሰራ ከርሟል፡፡ እነዚህ ሃሰተኛና የአንድ ወገን ዘገባዎች ደግሞ በምርጫው እንቅስቃሴ ላይ እክል እየፈጠረብን ነው፡፡ ይህ የጣቢያው ድርጊት የማይቆም ከሆነ ወደ ክስ መሄዳችን አይቀርም፡፡
“ፓርቲው የህብረተሰቡን መሪር ሃዘን ተጠቅሞ የራሱን አጀንዳ ለማስፈፀም ሲተጋ ነበር” ነው የተባለውና ከተጐጂ ቤተሰቦችና ከህብረተሰቡ የገጠማችሁ  ተቃውሞ አለ…
ኧረ ምንም አይነት ተቃውሞ አላጋጠመንም፡፡ እኛ እንደ ዶ/ር ቴድሮስ አድሃኖምና ከንቲባ ድሪባ ኩማ ሀዘንተኞችን አጽናንተናል ብለን ለሚዲያ ፍጆታ ባናውለውም፣ አመራሮቻችን ሃዘንተኞቹን  በየቤታቸው በመገኘት አጽናንተዋል፡፡
እንደውም በአጋጣሚ ከሠማያዊ ፓርቲ የመጣን አልመሠላቸውም ነበርና ሠማያዊ ፓርቲዎች እንዴት ነው ያላፅናኑን የሚል ሃሜት እዚያው ቁጭ ብለን ስንሰማ ነበር፡፡ እናም የሟቾቹ ቤተሰቦች በጥሩ መንፈስ ነበር የተቀበሉን፡፡ አሁንም ፈጣሪ መጽናናቱን ይስጣቸው እንላለን፡፡
በሠልፉ ላይ የፓርቲው አመራሮችም ሆኑ አባላትና ደጋፊዎች የነበራቸው ተሣትፎ በምን መልኩ ነበር?
መንግስት ሠልፉን ቢጠራም እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ አይኤስ የፈፀመውን አሠቃቂ ግድያ ለማውገዝ አባሎቻችንና ደጋፊዎቻችን እንዲገኙ በዋዜማው ጥሪ አስተላልፈናል፡፡ ሠልፉን በሚገባ ደግፈን ነው የወጣነው፡፡
በሠልፉ ላይ መንግስትን ነው ወይስ አይኤስን ነው ለመቃወም የወጣችሁት? አጀንዳችሁ ምን ነበር?
በመግለጫችን ላይ ግልጽ አድርገነው ነበር፡፡ አይኤስ በወገኖቻችን ላይ የፈፀመውን አሠቃቂ ግድያ እንቃወም የሚል ነው፡፡ ሃዘናችሁን ለመግለጽና ድርጊቱን ለማውገዝ አደባባይ ውጡ ነው ያልነው፡፡ ከዚያ በተረፈ መንግስትን መቃወም የተጀመረው ረቡዕ ብቻ አይደለም፤ በዚህ ጉዳይ ቀደም ብሎ ተቃውሞ ሲገጥመው ነበር፡፡
ማክሰኞ እለት ሰው ራሱ ወጥቶ ነበር የተቃወመው፡፡ ማክሰኞ በራሱ የወጣው ህዝብ እኮ ነው ረቡዕ እለት በድጋሚ ተቃውሞውን ያሰማው፡፡ እኔ እንደሚገባኝ ተቃውሞ የተፈጠረው ማንም ስላደራጀው ሣይሆን መንግስት ከዚያ በፊት ይሠጣቸው በነበሩ መግለጫዎች የተነሳ ነው፡፡
“ኢትዮጵያዊነታቸውን እናጣራ፣ ህገወጥ ስደተኞች ናቸው” የሚሉት መግለጫዎች ሰው ያስቆጣል፡፡ የሰውን የቁጣ ስሜት የአንድ የፖለቲካ ፓርቲ አጀንዳ አድርጐ መግለጽ ተገቢ አይደለም
መንግስት ተቃውሞውን ሠማያዊ ፓርቲ ስለማቀነባበሩ ማስረጃ አለኝ እያለ ነው …
ይሄ አዲስ አይደለም፡፡ በኢህአዴግ ቤት የተለመደ ነው፡፡ የውሸት ማስረጃ ማቀነባበር የተለመደ ነው፡፡ የታሠሩት አምስት አባሎቻችን ሌሊት እንደሚመረመሩና በምርመራው ወቅትም ፓርቲውን እንዲለቁ ግፊት እንደሚደረግባቸው ሰምተናል፡፡ ለምሣሌ አመራራችን ወይንሸት ሞላ የተያዘችው ገና ሰልፉ ሣይጀመር ነው፡፡ እሷ ላይ ታዲያ ምን አደረገች ተብሎ ነው ማስረጃ የሚቀርብባት፡፡ በእለቱ ምን ያደረገችው ነገር አለ? ማስረጃ ብለው የሚያቀርቡት የውሸት ነገር በኢህአዴግ ቤት በሽበሽ ነው፡፡ የኛን ነገር ግን የሚፈርደው ታሪክ ብቻ ነው፡፡
በዚህ ሰሞን ደግሞ በክልክል ቦታዎች ላይ የቅስቀሳ ፖስተር ፓርቲው ለጥፏል በሚል ከምርጫ ቦርድ ማስጠንቀቂያ ደርሶታል፤ በእናንተ በኩል በዚህ ጉዳይ ላይ ያለው መረጃ ምንድነው?
ይሄ  ፓርቲው በጣም የተቸገረበት ጉዳይ ሆኗል፡፡ ለምርጫ ቦርድም ረቡዕ እለት ከኛ ቁጥጥር ውጪ እንደሆነ በመግለጽ ደብዳቤ ፅፈናል፤ በግለሰብ ደረጃ ሣይሆን በተቀነባበረ ደረጃ ይሄን ነገር የሚያደርግ አካል እንዳለም ተረድተናል፡፡
ስለዚህ ይሄን ምርጫ ቦርድ ተገንዝቦ ጉዳዩ ከአቅማችን በላይ በመሆኑ ክትትል እንዲያደርግልን ጠይቀናል፤ ነገር ግን ለደብዳቤው ትኩረት ሣይሰጡ መልሰው እኛኑ ነው እየከሰሱ ያሉት፡፡ በእኛ በኩል የተሠሩ ስህተቶችን እየፈለግን እያረምንም ነው፡፡ በጋራ መኖሪያ ቤት አካባቢ፣ በፕሮቴስታንት ቤተ እምነቶች አካባቢ ሣይታወቅ የተሠሩ ስህተቶች ሲያጋጥሙንም ፈጥነን እንዲነሣ እያደረግን ነው፡፡
ፖስተሮቻችን እየተቀደዱ ከመጣላቸውም በላይ በአንዳንድ ቦታዎች የተቀደዱት ከመሬት ተነስተው የተከለከሉ ቦታዎች ላይ ሆን ተብለው ተለጥፈው ተመልክተናል፡፡ እኛ በጭራሽ ያልተንቀሳቀስንባቸው አንዳንድ ቦታዎች ላይ ለምሳሌ በመስጊድ ላይ ተለጥፎ አይተናል፡፡ በአካባቢው ግን የኛ የቅስቀሳ ቡድኖች ድርሽም አላሉም ነበር፡፡
እነዚህን ችግሮች እንግዲህ ለቦርዱ አመልክተናል፡፡ ቦርዱ እርምጃ የማይወስድ ከሆነ ህብረተሰቡ እንዲከታተልልን ጥሪ እናቀርባለን፡፡
በእናንተ በኩል የደረሳችሁበት ምንድነው?
ሆን ብለው የፓርቲውን ስብዕና ለማጠልሸት የሚንቀሳቀሱ አካላት እንዳሉ ተረድተናል፡፡ ለዚህም ነው ለቦርዱ ከአቅማችን በላይ ሆኗል ብለን ደብዳቤ የፃፍነው፡፡ ቦርዱ ከኛ ጐን በመቆም ለህዝቡም ይሄን ነገር እንዲያሳውቅልን እንፈልጋለን፡፡
እስካሁን ያለው የቅስቀሳ ሂደታችሁ ምን ይመስላል?
በአራቱም የሃገሪቱ ጫፎች የቅስቀሳ ቡድን አሠማርተናል፡፡ ነገር ግን በአንዳንድ ቦታዎች ተግዳሮት እየገጠመን ነው፡፡ ለምሣሌ በአዋሣ አትቀሰቅሱም በሚል ከፖሊስ ተቃውሞ ገጥሞን ነበር፤ ነገር ግን አባሎቻችን ጉዳዩን አለዝበው በማየታቸው በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥም ቢሆን ቅስቀሳ ማድረግ ተችሏል፡፡ ግን የምርጫ ኮሚቴ አባላችን ሳምሶን ግዛው “በሞባይል ፖሊስ ፎቶ አንስተሃል” በሚል ፍ/ቤት ቀርቦ የ7 ቀን ቀጠሮ ተጠይቆበታል፡፡ እንግዲህ ፎቶ ማንሣትም ወንጀል ሆኖ፣ ዋስትናም አስከልክሎ ለእስር ዳርጓል ማለት ነው፡፡
ሌላው ምስራቅ ጐጃም እና ምዕራብ ጐጃም ላይ አስተባባሪዎቻችን ሣሙኤል አወቀ እና አዲሱ ጌታነህ ተደብድበውብናል፡፡ ለከፍተኛ ጉዳትም ተዳርገው ህክምና እየተከታተሉ ነው፡፡ ከዚያ በተረፈ የምርጫ ቅስቀሳ ፖስተሮች መቀደድ አንዱ ያስመረረን ጉዳይ ነው፡

Published in ህብረተሰብ

እንዴት ከረማችሁሳ!
ስሙኝማ…አውራ ጣት ለ‘ፊርማም’ ቢሆን ታገለግላለች፣ አመልካች ጣት…አለ አይደል… ያው ታመለክታለች፣ (“ትጠቁማለች…” “ታስበላለች…” ማለት ይቻላል፣) ቀለበት ጣት ጣጣ የላትም፣ ትንሸኛዋ ጣት ደግሞ ጥፍር ሲያድግባት ‘ጌጥ’ ትሆናለች (ቂ…ቂ…ቂ…)፡፡ እናላችሁ… እኛ አሁን ግራ የገባን የመሀል ጣት በየመኪናው መስኮት የምትሰቀለው “ጌጥ አላደረጉኝም… የቀለበት ጣት አላደረጉኝም...ጥፍሬን አላሳደጉልኝም…” ምናምን ነገር ብላ ነው እንዴ! አሀ… ግራ ገባና! ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታም አይደል…እነኚህ ‘ሲክስቲ፣’ ‘ሰቨንቲ’ ምናምኗን አልፈው እንኳን በመኪና መስኮት ‘እብሪተኛ’ መሀል ጣታቸውን የሚቀስሩትን ስታዩ… “ታዲያ ይሄኛው ትውልድ
ምን ይፈረድበታል!” አያሰኛችሁም?
ከ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይሰውረንማ!  
ሀሳብ አለን… ለአቅመ አዳምና ለአቅመ ሔዋን የደረሱ ሰዎች ‘እብሪተኛ’ መሀል ጣታቸውን በመስኮት ብቅ አድርገው ‘ሰንደቃቸውን’ ሲተክሉ ፎቶ ብልጭ አድርጎ ለልጆቻቸው…. “እየውልህ፣ አባትህ አንዲህ አይነት ሰው ነው…” “የእናትሽን ጉድ ተመልከቺ…” የሚባል ቢሆን ሳይሻል አይቀርም። ልክ ነዋ… ሌላው ላይ በተነጣጠረች ‘እብሪተኛ’ መሀል ጣት እኛም ለምን እንሳቀቃለን!
ስሙኝማ…እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… የ‘እብሪተኛ’ መሀል ጣት ነገርን ካነሳን አይቀር ምን መሰላችሁ…ብዙ ቦታዎች ከ‘መሀል ጣት እብሪት’ የማይተናነሱ ነገሮች እያየን ነው፡፡ የምር ግን…እዚህ አገር የሞራል እሴቶቻችንን፣ የ‘ጨዋነት’ ምልክቶቻችንን ሁሉ ቀርጥፎ የበላብን ነገር ምን እንደሆነ እሱ ይወቀው፡፡
ከ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይሰውረንማ!  
ስብሰባ የጠራ ‘ጉልቤ ነገር’ ሥራ አስኪያጅ ወይ የምናምን ተጠሪ ተሰብሳቢዎቹን በቅጡ እንኳን…

“እንደምን አደራችሁ…የጎን ውጋት አስቸገረን ያላችሁት ጠበሉ ሠራላችሁ ወይ…” ምናምን ነገር ሳይል… አለ አይደል… “አንዳንድ ሠራተኞች የድርጅቱን ምርታማነት ለማዳከም ሆነ ብለው…” ምናምን ብሎ ስብሰባውን በ‘መሀል ጣት እብሪት’ አይነት ይጀምረዋል፡፡ ጉዳይ ማስፈጸሚያ መሥሪያ ቤት በር ላይ ያለው ‘ሴኪዩሪቲ ጋርድ’  (በ‘ፈረንጅ አፍ’ ሲሆን ሞቅ ያደርገዋል ብዬ ነው) መጀመሪያ ከእግር እስከ ራሳችሁ ይገላምጣችኋል፡፡ ከዛማ ‘ከመጤፍም ስለማይቆጥራችሁ’… አይደለም በስነ ስርአት መልስ ሊሰጣችሁ… ጀርባውን ያዞርባችኋል፡፡
(እንትና…ያቺ ሰሞኑን ጎንህ አድርገህ የምትዞራት ግድንግዷ እሷዬዋ፣ ‘ሴኪዩሪቲ ጋርድህ’ ነች እንዴ!…ነው ወይስ በአንድ በኩል ‘ለጥበቃ’፣ በሌላ በኩል ‘ለእነሆ በረከት’ ሁለት ወፍ በአንድ ድንጋይ መምታትህ ነው! ቂ…ቂ…ቂ…) እናላችሁ… ‘ሴኪዩሪቲ ጋርዱ’ ምንም ቃል ሳይተነፍስ በግልምጫ ብቻ የ‘መሀል ጣት እብሪት’  ያሳይችኋል፡፡የዕድሩ ዳኛ…ገና እንቅልፋቸው ሳይለቃቸው እየተንጠራሩ “በስንት ልፋት የተቋቋመውን ዕድር
ለማፍረስ አንዳንድ አባላት ወርሀዊ መዋጮአቸውን ባለመከፈል ችግር እየፈጠሩብን ነው…” ምናምን
ይሉና ነገርዬውን… አለ አይደል… የ‘መሀል ጣት እብሪት’ አይነት ያደርጉታል፡፡‘ሰማይ ጥግ’ ያለው ባለስልጣን መልካም ሥራ ከሚሠሩት ብዙኃኑ ይልቅ፣ እሱ “እኩይ ተግባራት ይፈጽማሉ…” የሚላቸውን ‘ጥቂት ሰዎች’ እየጠቀሰ… “አንዳንድ ዕድገታችን ያልተዋጠላቸው…” ምናምን ብሎ የ‘መሀል ጣት እብሪት’ ነገር ያደርገዋል፡፡
ከ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይሰውረንማ!  እግረ መንገዴን ይቺን ስሙኝማ…ለማኙ የሆነች ሸላይ ሴትዮ ‘ቶርታ’ ምናምን ነገር ጠቅልላ ስትሄድ ትገጥመዋለች፡፡ እናማ… “የእኔ እመቤት እንደው ኬክ ብትመጸውቺኝ…” ይላል፡፡ እሷዬም በሸላይኛ በዓይኗ እንትን ታየውና… “ኬክ! ደሞ ለራበው ሰው ዳቦ አነሰው እንዴ!” ትለዋለች፡፡ እሱዬው ምን ቢል ጥሩ ነው…“ምን መሰለሽ ዛሬ ልደቴ ነው፡፡” እንዲህም ይለመናል፡፡ ልክ እኮ… አለ አይደል…በፊት ጊዜ... “የሰው ጥርስ አውልቄ አስተክል ስለተባልኩ የተቻላችሁን እርዱኝ..” እንደሚሏት አይነት አለማመን ነች፡፡. እናላችሁ…ዛሬ ኬክ መጽውቱኝ ያለ ሰው ነገ ደግሞ ‘ሜኑ’ ይዞ ቢመጣ አትገረሙ፡፡
እኔ የምለው…እንደ ማኦ ዜዱንግ ዘመን ‘የባህል አብዮት’ ምናምን ሊያስፈልገን ነው እንዴ! አሀ…ነገርዬው ሁሉ ግራ ከመጋባትም እያለፈ ነዋ! የ‘መሀል ጣት እብሪት’ በተለያየ መልኩ ይከሰታል፡፡ ተናጋሪው ሁሉ፣ መግለጫ ሰጪው ሁሉ… የ‘መሀል ጣት እብሪት’ ስትራቴጂን ‘የሚተገብርበት’ (ቂ…ቂ…ቂ…) ጠላት ማግኘቱ ‘ኮምፐልሰሪ’ ምናምን የሚሉት አይነት ነገር ‘የጋራ ግንዛቤ የተወሰደ’ ይመስላል፡፡
ከ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይሰውረንማ!  
የምር ግን ‘የባህል አብዮት’ ምናምን አይነት ነገር ቢፈጠር አንዳንድ ወዳጆቻችን ታዩኝ፡፡ እዚህ አገር እኮ የዕድሜ ልዩነት…ጉርምስና፣ አቅመ ዓዳም፣ አቅመ ሔዋን ቅብጥርስዮ ምናምን የሚል ነገር የቀረ ይመስላል፡፡ ልክ ነዋ…ለምሳሌ ጉርምስና ምናምን የሚባለው ነገር በአሥራ አንድም፣ በሠላሳ አንድም፣ በስድሳ አንድም ሊሆን ይችላል፡፡ አቅመ ሔዋን ምናምን የሚባለውም በአሥራዎቹ ወደታች እየወረደ… አለ አይደል…‘ማሙሽ’
‘ማሚቱ’ ማለት የሚቻለው የትኛው ዕድሜ ላይ እንደሆነ ግራ እየገባን ነው፡፡እናላችሁ…‘የባህል አብዮት’ የሚባለውን ነገር ቻይኖቹ ሹክ ያሉን ቀን ‘ሶሻል ሜዲያ’ ቀለጠ ማለት ነው፡፡… ስሙኝማ…የቻይናን ነገር ካነሳን አይቀር…አንዳንድ ቦታ በቻይንኛ ብቻ የተጻፉ ምልክቶች ምናምን እያየን ነው፡፡ ነገ ደግሞ ምናምን በሆነ ሬዲዮ ላይ የቻይንኛ ዝግጅት ክፍል የሚባል በቀን የአራት ሰዓት ምናምን ፕሮግራም ይጀመር ይሆናል፡፡ የምር ግን… የቀለጠ ፍቅራችንን ክፉ ዓይኖች እንዳያዩብን እዛው ይያዝልን፡፡ ልክ ነዋ…በኋላ ነገርዬው “ፍቅሬ ፍቅሬ በዛ፣ እኔ አላማረኝም…” ምናምን ነገር ያመጣላ! ከዛማ ያው የማይቀረው የ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይመጣል! “ድሮስ እነሱን ብሎ ወዳጅ! የምንተነፍስውን ኦክሲጅን እንኳን ቢመቻቸው በ‘ፎርጀሪ’ ይሠሩት ነበር!”“ሀበሻ ሆዱ አይታወቅ፣ ልቡ አይታወቅ…ምስር ወጣቸውን በላንላቸው፣ ካቲካላቸውን ጠጣንላቸው!
እንትናዬዎቻቸው የቱሪስት ሂሳብ የሚጠይቁን ለምንድነው!”
ምናምን መባባል ይመጣል፡፡ ይህ “ዓይናችሁ ለአፈር…” ምናምን መባባል ደግሞ ‘ታሪካዊ ሀቅ’
ምናምን ነው ማለትም ይቻላል፡፡ ከስንቱ ጋር… “እኛም አንድ ሰሞን እንዲህ አርጎን ነበር…” ስንባባል

ኖረን የለ!
ከ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይሰውረንማ!  ሀሳብ አለን… “ቅዳሜ ለእነሆ በረከት ይመችሻል ወይ…” “ሰውዬሽ ፊልድ የሚወጣው መቼ ነው…”
“የጓደኛዬ አክስት አርፈው የሠልስት አዳር አለብኝ ብለሽ ውጪ…” ምናምን አይነት ነገሮች በቻይንኛ
ምን እንደሚባሉ በ‘ዩቲዩብ’ ይለቀቅልንማ! እኛ ‘የቸገሩንን’ ነገሮች መች አጣናቸው! (የምር ግን…
ይሄኔ በቻይንኛ የ‘መሀል ጣት እብሪት’ ቃላትን የሚያውቅ መአት ሰው ይኖራል፡፡) እናላችሁ…የባህል አብዮት ምናምን የሚል ነገር ቢመጣ ‘ስታንድ አፕ’ ኮሜዲ በአዳራሽና በምሽት ክበብ ሳይሆን በየመንገዱ ይሆን ነበር፡፡ እናላችሁ…እኛ መሬት የሚጠርግ ሱሪ አጥልቀን እነሱ የዋናተኛ ሙታንቲ ልታክል ምንም ባልቀራት ቁምጣ ሲሄዱ ያላሰብነውን የሚያሳስቡን መአት ናቸው! ልክ ነዋ… አንድ አገር ተመሥርታ መካከለኛ ገቢ የምታልፍበት ዘመንን ያህል ‘ፉት’ አድርገው እንደ ‘ቲንኤጀር’ ሲያደርጋቸው የእኛ ኪሎ በመሳቀቅ መቀነሱ እየቀረ ነው! የምር እኮ…ቀለም እየተቀቡ ‘ዩዝ’ ምናምን ለመምሰል መሞከር ‘ያለፈበት ስትራቴጂ’ እየሆነ ነው፡፡ እናላችሁ…‘መሀል ጣት እብሪት’ ነገርም የሁላችን የጋራ መለያ ነገር እየሆነ ነው!   ከ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይሰውረንማ!   ‘ባለፈው ስርአት’ ጊዜ በሥራ ሰዓት ጠጅ ሲጠጣ የተገኘ ሰው ጭንቅሌው ላይ ብርሌ ተሸክሞ በየመንደሩ እየዞረ… “እኔን ያያህ ተቀጣ!” እያለ ይዞር ነበር፡፡ እናላችሁ… የ‘መሀል ጣት እብሪት’ ነገር
እየበዛ “እኔን ያያህ ተቀጣ!” ምናምን የሚያሰኙ ነገሮች በዝተዋል፡፡ እናማ… ምን ይመስለኛል መሰላችሁ… የ‘መሀል ጣት እብሪት’ ከመብዛቱ የተነሳ ትንሽ ቆይቶ በምንም ነገር ላይ መግባባት ሁሉ ያቅተናል፡፡ እንኳን ሌላ ተጨምሮብን አሁንም መግባባት አቅቶናል፡፡ ይቺን ስሙኝማ…ልጁ አባቱን ይሄን ያህል አይወደውም ነበር፡፡ እናማ…አንድ ቀን ለአባቱ እንዲህ ይለዋል፡፡“አባዬ፣ ውሻዬን ሼክስፒር ብዬ ልጠራው ፈልጌ እማዬ ከለከለችኝ…” ይለዋል፡፡ አባትዬውም…“ለምን ከለከለችህ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡“ሼክስፒርን መስደብ ይሆናል አለችኝ፡፡” “እና ምን አሰብክ?”“በአንተ ስም ልጠራው ፈልጌ እማዬ ከለከለችኝ።”“ለምንድነው የከለከለችህ?”
“የአንተን ስም መስጠቱ ውሻውን መስደብ ይሆናል አለችኝ፡፡” አሪፍ አይደል!... የ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይሏችኋል እንዲህ ነው፡፡
ከ‘መሀል ጣት እብሪት’ ይሰውረንማ!  
ደህና ሰንብቱልኝማ!

Published in ባህል

“አሁንም እንሄዳለን፤ምንም ተስፋ የሚሰጥ ነገር የለም”
ኢህአዴግ ከስንት አንዴ ፕሮፓጋንዳው ቢቀርበትስ?

  መንግስት አይኤስ የተባለውን ጨካኝና አሸባሪ ቡድን ለማውገዝ የጠራው የተቃውሞ ሰልፍ እንደ አጀማመሩ አልተጠናቀቀም፡፡ (ለተቃውሞ ወጥቶ ተቃውሞ ገጥሞታል!) በሰላም የተጀመረው ተቃውሞ በረብሻና በብጥብጥ ተቋጨ፡፡ (መንግስትን መቃወም እኮ መብት ነው!) ትንሽ ቅር ያለኝ ግን ምን መሰላችሁ? ሁለት ተቃውሞዎች በአንድ ቀን፣ በአንድ ቦታ፣ መደረጋቸው ነው፡፡ እንደኔ ቢሆን ሁለቱ ተቃውሞዎች ባይደባለቁ እመርጥ ነበር (የሚያስመርጥ ሲኖር አይደል!) አንዳንዴ ተቃውሞ ፋታ አይሰጥም መሰለኝ፡፡ ተቃውሞ የነበራቸው ወገኖች የዚያኑ ዕለት መቃወሙን ግን ለምን ፈለጉት? ምናልባት ሌላ ቀን የሰልፍ ፈቃድ የሚሰጠን የለም ብለው ይሆናል (በስጋት ማለት ነው!) ወይም ደግሞ ጠ/ሚኒስትሩን ጨምሮ ትላልቅ ባለስልጣናትን መስቀል አደባባይ ሲያዩ፣ መንግስትን ለመቃወም ከዚህ የተሻለ ቀን ሊኖር አይችልም ብለውም ሊሆን ይችላል፡፡ ስለዚህ ዕድሉን ተጠቀሙበት ማለት ነው፡፡ ግን እኮ---መንግስት የጠራውን ሰልፍ ረቡዕ፣ መንግስትን ለመቃወም ደግሞ ሐሙስን መጠቀም ይቻል ነበር (“ፈቃድ” ይገኛል በሚል ተስፋ ማለት ነው!) ያውም ደግሞ ያለ ወከባና ያለ ድንጋይ ውርወራ--! ግን በቃ የመሰላቸውን አደረጉ፡፡ ሌላው ጥያቄ ምን መሰላችሁ? ተቃውሟቸው በትክክል መንግስት ጋ ደርሷል? በነገራችን ላይ ፖሊስ ሰልፉን ለመበተን ጥይት ከመጠቀም ይልቅ አስለቃሽ ጭስ መጠቀሙ ሥልጣኔ ነው፡፡ (ጭሱ በእርዳታ ነው በግዢ?) የአንዳንዶቹ ፖሊሶች ድብደባ ግን ከጥይት አይተናነስም ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ ለማንኛውም በፖሊስ እጅ ገብታችሁ ዱላ ከበዛባችሁ፤ “ወገን ነን!” ማለቱን እንዳትረሱ፡፡(በሥራ ብዛት ልትረሱ ትችላላችሁ!) ሰሞኑን በጫማ ጥፊ የሚማታ ፖሊስ ፌስ ቡክ
ላይ ተለጥፎ አይቼ ክፉኛ ደንግጬ ነበር፡፡ (“ተስፋ የለንም!” በሚል) የተረጋጋሁት  የኔፓል ፖሊስ መሆኑን ስሰማ ነው፡፡ (አደራ የኔፓል ፖሊስን ተመክሮ እንዳትወስዱ!) እኔ የምለው-- በረቡዕ ሰልፍ ላይ የተነሳው ተቃውሞ ምን ነበር ? (የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት ትንፍሽ አላለም ብዬ ነው!) እንግዲህ እስካሁን የሰማነው “የተቃውሞው አደራጅ ሰማያዊ ፓርቲ ነው” የሚል ክስ ብቻ ነው፡፡ (ፓርቲው በበኩሉ፤መንግስት ስሜን እያጠፋ ነው፤እከሳለሁ ብሏል!) በዚህ አጋጣሚ ግን ለመንግስትም ሆነ ለኢህዴግ አንድ ምክር በወንድምነት ብለግሳቸው እወዳለሁ፡፡ ከወገኖቻችን ግድያና ስደት ጋር በተገናኘ መንግስት ላይ የተሰነዘሩ ትችቶችና ተቃውሞዎች ካሉ (እሱማ የት ይጠፋሉ!) ሸፋፍኖ ማለፍ አይመክርም፡፡ ይልቁንም “ጉዱን” በደንብ
ሰምቶ፣ እሱም የራሱን በደንብ አስረድቶ፣ ወደ መፍትሄ መግባት ብልህነት ነው፡፡ ይሄ የስደት ጉዳይ በጊዜ መላ ካልተበጀለት ጊዜ ጠብቆ የሚፈነዳ ቦንብ ነው፡፡ (ደሞ ጀማምሮታል!) መንግስት ዜጎች ዘንድ “ብዥታ” አለ ብሎ የሚያምን ከሆነ፣ ማጥራት የሱ ሃላፊነት ነው፡፡ የአመለካከት ችግር ነው የሚል ከሆነም አመለካከት ላይ መሥራት ይኖርበታል፡፡ እንደ እስከዛሬው  ነገሩን ሁሉ በ“ህገወጥ ደላላ” ላይ አሸክሞ መቀመጥ አያዋጣም፡፡ (አዝማሚያው እንደዛ ይመስላል!) በነገራችን ላይ ባለፈው እሁድ አርቲስቶች በግፍ ለተገደሉ ወገኖቻችንን መታሰቢያ በብሔራዊ ቴአትር ባዘጋጁት ፕሮግራም “ህገወጥ ደላሎች” ላይ የእርግማን መዓት ሲያወርዱ ነበር (እርግማን እንደ ግጥም ጽፈው!) እውነቱን ለመናገር ግን አሁን የሚያስፈልገው እርግማን ሳይሆን እርምጃ ነው!
እኔ የምለው ግን----እስካሁን የተያዘ አንድ እንኳን ህገወጥ ደላላ አለ ወይስ ዝም ብለን ነው እርግማን  የምናወርደው? (እርግማን እኮ ውጤት ተኮር አይደለም!)  በነገራችን ላይ አንዳንድ የማይገቡን ወይም እንዳይገቡን የተደረጉ ነገሮች ያሉ ይመስለኛል፡፡ የናንተን ባላውቅም----እኔ ግን ይሄ የስደት ጉዳይ ሁሌም ግራ እንዳጋባኝ ነው፡፡ የስደት ጉዳይ በተነሳ ቁጥር መንግስት ለአፍታ እንኳን ማሰብ ሳያስፈልገው መልስ ይሰጣል - “ዜጎች በአገራቸው ሰርተው መክበር እየቻሉ ነው ስደት የሚሄዱት” በማለት በቀላሉ ይዘጋዋል፡፡ እኔና እናንተ ግን ግራ ይገባናል፡፡ ዜጎች እንደጉድ መሰደዳቸው፣ ባህር ውስጥ እየተጣሉ የዓሳ ነባሪ እራት መሆናቸው፣ በደላሎች መሰቃየት መታለላቸው፣ በረሃብና በጥማት በየበረሃው መቅረታቸው---እነዚህን ሁሉ መከራዎች የሰሙ ዜጎች  ምንም እንዳልሰሙ ሆነው ለስደት ሲነሱ -- ለሞት ሲዘጋጁ፣ ግራ ያጋባል፡፡ ማናችን ነን የተሳሳትነው? እኔና እናንተ? እነሱ? ወይስ መንግስት?  ሰሞኑን የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጽ/ቤት በድረገጹ ላይ ባወጣው መግለጫ፤በአሁን ሰዓት የኢትዮጵያውያን ዓመታዊ የነፍስ ወከፍ ገቢ ወደ 630 ዶላር ግድም መሆኑን ጠቁሞ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ወደ 1ሺ ዶላር እንደሚደርስ አስታውቋል፡፡ (መንግስት ቁጥሩን በኑሮ እየመነዘረ ይንገረን!) ለምሳሌ የነፍስ ወከፍ ገቢያችን 630 ዶላር በመሆኑ፣ በህይወታችን ላይ ከበፊቱ ምን
ጨመርን? ወደ 1ሺ ዶላር ስንገባስ ለውጣችን ምን ይሆናል? (ቁጥሩ ቀርቶ ተጨባጩ ኑሮ ብቻ!) መንግስት ስደትን በተመለከተ በዜጎች ዘንድ የአመለካከት ለውጥ እንደሚያስፈልግ በተደጋጋሚ ሲናገር እንሰማለን፡፡ ስህተት የለውም፡፡ በእርግጥም የአመለካከት ለውጥ ያስፈልጋል፡፡ አሁን ሳስበው መጀመሪያ የአመለካከት ለውጡ የሚያስፈልገው ለራሱ ለመንግስት ነው፡፡ አንዳንዴ ምን እላለሁ መሰላችሁ? “መንግስት የሚነግረን የሚመኘውን ነው ወይስ መሬት ላይ ያለውን እውነታ?” ቆይ እሱ እንደሚለው ዜጐች በአገራቸው ሰርተው መክበር የሚችሉ ከሆነ፣ ለምንድነው ወደ ሰው አገር የሚጎርፉት? ለምንድነው ወደ ሞት የሚጋፉት? ለምንድነው የበረሃ ሲሳይ ለመሆን የሚጣደፉት? መቼም ምክንያት መኖር አለበት፡፡ መንግስት ይሄን ጉዳይ ከፖለቲካና ፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ውጭ በጥልቀት አጥንቶና አስጠንቶ ወደ መፍትሄው ለመቅረብ መትጋት አለበት፡፡   ባለፈው እሁድ በወጣው ሪፖርተር ጋዜጣ ላይ ያነበብኩት ነገር ክፉኛ አስደንግጦኛል፡፡ ጓደኞቻቸው ሊቢያ በሚገኘው አሸባሪ ቡድን በግፍ የተቀሉባቸው የጨርቆስ ወጣቶች፣ አሁንም የስደት ሃሳባቸውን እንዳልቀየሩ ለጋዜጣው ተናግረዋል፡፡ አንደኛው ወጣት፤ “አሁንም እንሄዳለን፤ምንም ተስፋ የሚሰጥ ነገር የለም፤እድላችንን እንሞክራለን”፣ሁለተኛወ ወጣት፤ “ህገወጥ ስደተኞች አትበሉ፤ ልጆቹ ህገወጥ አይደሉም፤እንጀራ ፈላጊ ናቸው”ሦስተኛው ወጣት፤ “ስብሰባ ጠርተው ሃምሳ ሃምሳ ብር ሰጥተው፣ ወጣቱ እየሰራ ነው የሚል ፕሮፓጋንዳ ከሚሰሩብን ምን አለ ስራ ቢፈጥሩልን?” (ወጣቶቹን ያነጋገረው የሪፖርተር ጋዜጠኛ፤ሁሉም በተስፋ መቁረጥ መንፈስ ውስጥ እንዳሉ ነው የገለጸው፡፡) ለማንኛው ግን መንግስት ለስደት ጉዳይ መፍትሄ ለማበጀት ከመነሳቱ በፊት ራሱን እንዲህ ብሎ ይጠይቅ፤  “ዜጐቼ ከገዛ አገራቸው የሚሰደዱት ለምንድን ነው?”  

     የቲያትር ትምህርቷን በከፍተኛ የትምህርት ተቋም ለመከታተል ከትውልድ አገሯ ባሌ፣ አጋርፋ አካባቢ የመጣችውን ለምለም ኃይለሚካኤል (ሚሚ)፣ በጥልቅ የሙዚቃ ፍቅሯ የተነሳ በ“ኢትዮጵያን አይድል” ለመወዳደር የትውልድ ቀዬዋን ጅማን ለቅቃ አዲስ አበባ የገባችው ጠሪፍ ካሣሁን (ሜላት) እንዲሁም እዚሁ አዲስ አበባ ተወልደው ያደጉት ራሔል ጌቱ (ለምለም)፣ እየሩሳሌም ቀለመወርቅ (ሣራ) እና ዘቢባ ግርማ (እሙዬን) ያገኘኋቸው እንደ ብርቅ ከሚታዩበት የአማራ ክልል ደብረታቦር ከተማ ውስጥ ነበር፡፡
“የኛ” በሚል ስያሜ የሚታወቀው ፕሮጀክት፤ በኢመርጅ ሊደርስ ኮንሰልታንሲ ትሬይኒንግ፣ በማንጐ ፕሮዳክሽንና በዴሎይት ኮንሰልቲንግ በተቋቋመው ኮንሰርቲየም የሚተዳደር ሲሆን በእንግሊዝ መንግስት የልማት ድርጅት (ዲኤፍአይዲ) እና በናይክ ፋውንዴሽን ትብብር በገርል ሀብ ኢትዮጵያ የገንዘብ ድጋፍ የሚከናወን ነው፡፡ ፕሮጀክቱ እነዚህ አምስት ወጣት ሴቶች የተወኑበትን አዲስ ፊልም ሰሞኑን በጥንታዊቷና ታሪካዊቷ የደብረታቦር ከተማ አስመርቋል፡፡ ከአዲስ አበባ በ666 ኪሎ ሜትሮች ርቀት ላይ የምትገኘው የደብረታቦር ከተማ ነዋሪዎች በ11 ሰዓት ላይ ለሚከናወነው የፊልም ምረቃ ፕሮግራም ገና በስምንትና ዘጠኝ ሰዓት ላይ ሥፍራውን አጨናንቀውት ነበር፡፡
የአካባቢው ህብረተሰብ ሣምንታዊውን የ “የኛ” የሬዲዮ ድራማና የአምስቱን ወጣቶች ሙዚቃ አጥብቀው የሚከታተሉና በእጅጉ የሚወዱ እንደሆኑ ሁኔታቸው ይመሰክራል፡፡ እስካሁን በሬዲዮ ድራማቸው የሚያውቋቸውና የሚያደንቋቸው ገፀባህሪያት፡- ሚሚ፣ እሙዬ፣ ለምለም፣ ሣራና ሜላት ፊልም ሲሰሩ ደሞ ለማየት እጅግ የጓጉ ይመስላሉ፡፡ ህፃን አዋቂው በሁለት ትላልቅ የፊልም ማሳያ ስክሪኖች ለእይታ የሚበቃውን ፊልም ለማየት አሰፍስፏል፡፡ የሁለትና የሶስት ሰዓታት የእግር ጉዞ አድርገው ከሥፍራው የደረሱ ወጣቶችም ነበሩ፣ እነዚህ አምስት ወጣቶች በአካባቢው ያተረፉትን እውቅናና በህብረተሰቡ ላይ የፈጠሩትን ስሜት ማወቅ እምብዛም አስቸጋሪ አይደለም፡፡ ይህም ፕሮጀክቱ የተቀረፀበትን ዓላማ ተግባራዊ እያደረገ ለመሆኑ ማሳያ የሚሆን ነው፡፡ በሥፍራው እየተዘዋወርኩ ያነጋገርኳቸው ወጣቶች፣ ታዳጊዎችና አዋቂዎች ስለየኛ፣ ስለድራማዎቹና ዘፈኖቻቸው በሚገባ ያውቃሉ፡፡ ፕሮጀክቱ ትኩረት አድርጐ በሚንቀሳቀስባቸው የሴቶች ጥቃት፣ ያለዕድሜ ጋብቻና አስገድዶ መድፈር በስፋት በሚታይባቸው የአማራው ክልል አካባቢዎች ሴቶች ልጆችን ወደኋላ ከሚያስቀሩ አስተሳሰቦችና ተግባራት አላቆ ማህበራዊ ለውጥን ለማምጣት የተቀረፀ ሲሆን የሬዲዮ ፕሮግራሙ በአካባቢው እጅግ ተደማጭ መሆኑን ለማወቅ ችያለሁ፡፡
በአምስቱ ወጣት ሴቶች የተሠራው ፊልም ምረቃ ሲጠናቀቅ ወጣቶቹን ለማየት፣ ከተቻለም በእጅ ለመንካት የአካባቢው ወጣቶችና ህፃናት ያሳዩት የነበረው ሁኔታ እጅግ ስሜት የሚነካ ነበር፡፡ የዩኒቨርሲቲ ተማሪ የሆኑ ወጣት ሴቶችም አምስቱ ወጣቶች ያረፉበት ሆቴል ድረስ በመሄድ ለወጣቶቹ ስሜታቸውን የገለፁበት ሁኔታ አስገራሚ ነው፡፡
ሰሞኑን በሊቢያ በወገኖቻችን ላይ የደረሰውን አሰቃቂ ግድያ ተከትሎ በመገናኛ ብዙሃን በተደጋጋሚ የሚሰማው  በእነዚህ አምስት ወጣቶች የተሰራው የስደት ዘፈን የፊልሙ አካል ሲሆን የተመልካቹን ስሜት  በእጅጉ የነካ ነበር፡፡
እሩቅ ማዶ እሩቅ አገር ሄዳለች
እታበባ ውብ አለሜ የት አለች
በእኔ እድሜ ነበር የተላከችው
ከማታውቀው አገር የተሸኘችው
እንኳን ጠረኗ ጠፍቶ ትንፋሿ ነው
የእሷ እጣ ታሰበ ለእኔ ለታናሿ፡፡
የሚል ስንኝ ያለው ዘፈኑ፤ የስደትን አስከፊነትና መራራነት አጉልቶ የሚያሳይ ነው፡፡ ከፈልም ምረቃው በኋላ ከ5ቱ ወጣቶች ጋር በጅማሬያቸው፣ በህልሞቻቸው፣ በተስፋዎቻቸውና በገጠመኞቻቸው ዙሪያ ጥቂት አውግተን ነበር፡፡
    
      ለፕሮጀክቱ እንዴት ታጫችሁ?
ለፕሮጀክቱ የታጨነው የተሰጠውን ፈተና ተወዳድረንና አልፈን ነው፡፡ አምስታችን ከመመረጣችን በፊት ለውድድር የቀረብነው 69 የምንሆን ልጆች ነበርን፡፡ ውድድሩ በ3 ዙሮች የተሰጠ ሲሆን ይህንን ሁሉ አልፈን ነው የተመረጥነው፡፡
ወደ ሥራው ስትገቡ እንዲህ አይነት ዓላማ ያለው ሥራ እንደሆነ ታውቁ ነበር?
ሥራው ሲጀመር እንዲህ ዓይነት ፕሮግራም መሆኑን አናውቅም ነበር፡፡ አንድ ተከታታይ የሆነ የሬዲዮ ድራማ እንደሚሰራ ነበር የምናውቀው፡፡ ሥራው የሴቶችን አቅም ለማጎልበት የሚያስችል ፕሮጀክት እንደሆነና ሙዚቃ ያለው ድራማ ያለው እንደሆነ የተነገረን ወደ ሥራው ከገባን በኋላ ነው፡፡ ከዛ ሥራውን በሚገባ ተገንዝበን እኛም እራሳችን የፕሮጀክቱ አባል ሆንን፡፡
የ“ኛን” ከተቀላቀልን በኋላ የመጀመሪያዎቹ 6 ወራት ከምንሰራው ነገር ጋር በደንብ እንድንተዋወቅና እንድንዋደድ የተደረግንበት ጊዜ ነበር፡፡ ይህም የምንሰራውን ሥራ በሚገባ እንድናውቀው፣ እርስ በርሳችንም በደንብ እንድንተዋወቅ ረድቶናል፡፡ የስድስት ወራት የልምምድ ጊዜያችን ሲጠናቀቅ ሁላችንም ቀደም ሲል ከነበረን አስተሳሰብ በእጅጉ ተለወጥን ነበር፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የትወና፣ የሙዚቃና የድምፅ ስልጠናዎች በብቁ ባለሙያዎች ይሰጠን ነበር፡፡ በድራማው ላይ ወክለን የምንተውናቸውን ገፀ ባህሪያት በድንብ እንድናውቃቸውና እንድንለምዳቸው ለማድረግ ከገፀባህርይው ጋር ተመሳሳይነት ካላቸው ሰዎች ጋር እንድንውል ተደርገናል፡፡ ይህ ደግሞ እጅግ የቀየረንና ሥራው በድንብ ስሜት ሰጥቶን እንድንሰራው አድርጐናል፡፡
ስለሴቶች ጥቃትና ችግር የነበረን ግንዛቤ እንደአብዛኛው የህብረተሰብ ክፍል ነበር፡፡ ስለጉዳዩ በየሚዲያው የሚነገረው አሰልቺ በሆነ መልኩ ስለነበር፣ ጆሮ ሰጥተን ለማዳመጥና ግንዛቤ ለመጨበጥ አልቻልንም ነበር፡፡ ነገር ግን “የኛ” ይህንን ቀየር አድርጎ ሳቢና አዝናኝ በሆነ መልኩ፣ የሰዎችን አስተሳሰብ ሊለወጥ የሚችል ፕሮግራም ቀርፆ ወደ ሥራ በመግባቱና እኛም የዚህ ፕሮጀክት አባል በመሆናችን እጅግ ደስተኞች ነን፡፡
የፕሮግራሙን ዓላማ ምን ያህል ተረድተነዋል ብላችሁ ታስባላችሁ?
ሴት ልጆችን ወደ ኋላ የሚያስቀሩ አስተሳሰብና ተግባራት በስፋት በሚታይባቸው አካባቢዎች እነዚህን ተግባራት ለማስቀረት የሚችልና ሴቶችን በማስተማር ማህበራዊ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችል ዓላማን ይዞ የተጀመረ ፕሮጀክት መሆኑን እናውቃለን፡፡ ማህበረሰቡ የአስተሳሰብ ለውጥ በማምጣት፣ ሴት ልጆችን ማበረታታት መደገፍና ማስተማር እንደሚገባው የማስተማርን ዓላማ ይዞ የሚንቀሳቀስ ነው፡፡ ሴት ልጆች የሚገጥማቸውን እንቅፋት ስናስወግድና እነሱን ስናበረታታ የምንለውጠው የእነሱን ህይወት ብቻ ሳይሆን የማህበረሰቡንም ጭምር ነው የሚል ዓላማ ያለው መሆኑን እናውቃለን፡፡
ይህንን ዓላማ ለማሳካት ጥረታችሁ ምን ያህል ነው? የእናንተስ አመለካከት ምን ያህል ተለውጧል?
ወደ ሥራው ከመግባታችን በፊት ባሉት ስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ ያገኘነው ልምድና ትምህርት እኛን ሙሉ በሙሉ የቀየረንና ስራው ወደ ውስጣችን ገብቶ እንዲዋሃደን ያደረገ ነበር፡፡ የስልጠናና የልምምድ ጊዜው ሲጠናቀቅ ሁላችንም በደንብ ነው የነቃነው፡፡ ጉዳቱ በቅድሚያ ለእኛ ሊሰማን ይገባል፡፡ እኛ በደንብ ሲሰማን ነው መልዕክቱን በሚገባ ለማድረስ የምንችለው፡፡ በዚያ የስድስት ወር ጊዜ ከምንሰራቸው ገፀ ባህርያት ጋር እንድንዋሃድ መደረጉ ለዚህ በጣም ጠቅሞናል፡፡ እያንዳንዱን ነገር አውቀነው ውስጣችን ተዋህዶ ነው የምንሰራው፡፡ እያንዳንዷ ከአፋችን የምትወጣው ቃል ምን ስሜት ይዛ አንደምትወጣ መገመቱ ከባድ ነው፡፡ አንድ ሥራ ስንሰራ ስንት ሚሊዮን ሴቶችን መቀየር እንደሚችል እያሰብን ነው የምንሰራው፡፡ የተሸከምነው ኃላፊነት ምን ያህል ከባድ እንደሆነም ይገባናል፡፡
በግላችሁ ከዚህ ፕሮጀክት አገኘነው የምትሉት ዕድልና በህይወታችሁ ላይ ያመጣው ለውጥ  ምንድነው?
ፕሮጀክቱ በግል ለእያንዳንዳችን ትልቅ እድል ነው፡፡ መንገድ ጠራጊያችን ነው፡፡ አስተሳሰብና አመለካከታችንን በሚገርም ሁኔታ ለመለወጥ እንድንችል ያደረገንም ነው፡፡ “የኛ” ከትልቅ ግንድ የተነሳና በርካታ ቅርንጫፎች ያሉት ዛፍ ነው፡፡ ሰፊ ቤተሰብ ያለው፣ ሁሉም በኃላፊነት ስሜት ሥራውን በመከባበርና በፍቅር የሚሰራበት ቤት ነው፡፡ ከዚህ ፕሮጀክት አባላት ጋር አብሮ መስራት በራሱ ትልቅ ዕድል ነው፡፡ ሲቀጥል ደግሞ በህይወታችን ህልም የሆኑብንና እንኳንስ አብረናቸው ልንሰራ ቀርቶ ለማየት እንጓጓላቸው ከነበሩ ታላላቅ ሙያተኞች ጋር ለመስራት መቻል የማይታመን እድል ነው፡፡ እንደ አይዳ አሸናፊ፣ ሰሎሜ ታደሰ፣ አስቴር አወቀ፣ አብርሃም ወልዴ፣ ፍቃዱ ተክለማርያም፣ ዓለማየሁ ታደሰና ኃይሌ ሩትን ከመሳሰሉ ታላለቅ ሙያተኞች ጋር ለመስራት መታደል ቀላል ነገር አይደለም፡፡ እነዚህ ሰዎች‘ኮ ህልሞቻችን ነበሩ፡፡ በተረፈ የሙዚቃና ትወና ችሎታችንን በማዳበር፣ ከሰዎች ጋር እንዴት ተግባብቶ መስራት እንደሚቻል ስለተማርንበት ቀላል የማይባል ጠቀሜታን ሰጥቶናል፡፡ ከዚህ ሁሉ በላይ ግን የራሳችን አስተሳሰብ እንዲቀየርና ስሜቱ እንዲሰማን በማድረጉ ረገድ ትልቅ ጠቀሜታ አለው፡፡ በቃላት ሊገለፅ የማይችልና ከአዕምሮ በላይ የሆነ ዕድል ነው ያገኘነው፡፡ ከዚህ በኋላ ምን ሊያቆመን ይችላል፡፡ ምንም አያቆመንም፡፡ ችግሩ የት ጋ እንዳለ፣ መንስኤና ምክንያቱ ምን እንደሆነና ችግሩን እንዴት መፍታት እንደምንችል እናውቃለ፡፡ እንዲህ ሙሉ እንድንሆን ያደረገን ደግሞ ይህ ፕሮጀክት ነው፡፡
እስከዛሬ በስፋት የምትታወቁት በሬዲዮ ድራማና በዘፈናችሁ ነው፡፡ አሁን ደግሞ ፊልም ሰርታችሁ አስመረቃችሁ፡፡ እንዴት ነው አዲሱ ሥራ አይከብድም?
ምንም አይከብድም፡፡ ፊልሙ ላይ የመጡት ያው የሬዲዮኖቹ ገፀባህሪያት ናቸው፡፡ ለእኛ አዲስ አይደሉም፡፡ ከሬዲዮ ድራማው ውስጥ ተቆርጦ የወጣ ታሪክ ነው ፊልም ሆኖ የተሰራው፡፡ እናም ብዙም አዲስ ነገር ሆኖ አላስቸገረንም፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሥራውን የሰራነው ከበቂ በላይ ዕውቀትና ልምድ ካላቸው ታላላቅ ባለሙያዎች ጋር በመሆኑ፣ ለእኛ ነገሮች እንዲቀሉና ሥራውን በአግባቡ እንድንሰራው አድርጎናል፡፡ ምንም የተቸገርንበት ነገር የለም፡፡
በሲኒማው ውስጥ የሚታየው ዘፈን ሰሞኑን በአገራችን ከተፈጠረው አስከፊ ሁኔታ ጋር ተገጣጥሟል፡፡ ይህ ለእናንተ ምን ስሜት ሰጣችሁ? ብዙ ሰዎች ዘፈኑ በቅርቡ በኢትዮጵያውያን ላይ በተፈፀመው አስከፊና ዘግናኝ ድርጊት መነሻነት እንደተሰራ ያስባሉ፡፡ እንዴት ነበር ሙዚቃውን የሰራችሁት?
ሙዚቃው የተሰራው በድራማው (በየኛ ድራማ) 4ኛ ሲዝን ላይ እሙዬ የተባለችው ገፀ-ባህርይ ኑሮ ከአቅሟ በላይ ሆኖባት፣ የቤተሰቧን ህይወት ለመለወጥ ወደ አረብ አገር ስደት የምትሄድበት ታሪክ አለ፡፡ በእሱ ምክንያት ነው ሙዚቃውን የሰራነው፡፡
ግን ፊልሙ ውስጥ እንዲካተት ተስማማንበትና አስገባነው፡፡ ለፊልሙ የተሰራው ሌላ ሙዚቃ ነበር፤ እኛ ግን ይህንን መረጥነውና እነሱም ተስማምተውበት ነው የገባው፡፡ ዘፈኑ በእያንዳንዳችን ቤት ውስጥ ያለ ኑሯችን ነው፡፡ ሲከፋሽ ብድግ አድርገሽ የምትሰሚው አይነት ነው፡፡ ስቱዲዮ ውስጥ ዘፈኑን ስንዘፍነው የምር “ፊል” እናደርግ ነበር፡፡ ሙዚቃው ሀዘንን ብቻ አይደለም የሚናገረው፤ ተስፋን፣ ራዕይን ሁሉ የሚያወራ ነው፡፡ ዘፈኑ አሁን ከተፈጠረው ነገር ጋር ሲገጣጠም ወይም ታሪኩ ውስጥ ገብቶ ስክት ሲል እንደ አዲስ ነው ያለቀስነው፡፡ ግጥምጥሙ በጣም አስገራሚ ነው፡፡ አገራችን አሁን የገጠማት ሀዘን ልብ የሚሰብር ነው፡፡ ግጥምጥሙ በደስታ ቢሆንና ዘፈናችን ተደማጭነትን ቢያገኝ ደስ ይለን ነበር፡፡
በዚህ ሥራ ላይ ከተሰማራችሁ በኋላ ወደተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የመጓዝና ከፕሮግራሙ (ድራማችሁ) ተከታታዮች ጋር የመገኘትና ዕድሉን አግኝታችኋል፡፡ በየሥፍራው ስትዘዋወሩና ከአድማጮቻችሁ ስትገናኙ የገጠማችሁ ለየት ያለ ነገር ነበር? ስሜታቸውስ ምን ይመስላል?
በአማራ ክልል የተለያዩ ሥፍራዎች ተዘዋውረናል፡፡ በዚህ ቦታ ያገኘነውን የህዝብ አስተያየትን ለመናገር ቃላት ያጥረናል፡፡ ህብረተሰቡ ሲወድሽ የእውነቱን ነው የሚወድሽ፡፡ የጆሮ ጌጥ፣ ሻሽ፣ የእጅ አምባር እየገዙ ስጦታ ይሰጡናል፡፡ እንጅባራ ውስጥ የእኛን ዘፈን ግማሹን በአገውኛ ቀይረውና ሚክስ አድርገው መድረክ ላይ ሲያቀርቡት ማመን ነው ያቃተን፡፡ የአምስትና የሰባት ሰዓት የእግር መንገድ እየተጓዙ ያለንበት ድረስ ይመጡም ነበሩ፡፡ እስቲ ልንካሽ፣ እስቲ ልንካሽ እስቲ ልቀፍሽ… ሲሉ ስሜት ይነካሉ፡፡ ፍቅራቸው ከምር ነው፡፡ “አንቺን መስማት ከጀመርኩ በኋላ ተስፋ ማድረግ ጀምሬ ህይወቴ ተቀየረ” ሲሉን በጣም ደስ ይለናል፡፡ “መንገድ ላይ ነው አይደል የምታድሪው?” ብሎ ሻርፕ ገዝቶ የሰጠን አድማጭም አለ፡፡ በደብረማርቆስ፣ በአንኮበር፣ በቡሬ ያጋጠመን የተመልካች አቀባበልና ስሜት በቃላት ሊገለፅ የሚችል አይደለም፡፡
ክፍያችሁ ከፍ ያለ እንደሆነ ይነገራል፡፡ ምን ያህል ነው?
 ስለክፍያ የተጋነኑ ነገሮች ሊወሩ ይችላሉ፡፡ ግን እውነታው እንደማንኛውም ጥሩ ተከፋይ ኢትዮጵያዊ አርቲስት፣ በጥሩ የወር ደመወዝ ተቀጥረን መስራታችን ነው፡፡ እኛ የየኛ” ብራንዶች ነን፡፡ ከዚህ የተለየ ሥራ መስራትም አንችልም፡፡ የተመረጥነው ትልቅ ዓላማ ላለው ሥራ ስለሆነ ማለት ነው፡፡ ስለዚህም ውጭ ያለው ሥራ እንዳያጓጓን የሚያደርግ ጥሩ ክፍያ እየተከፈለን እንሰራለን፡፡
ፕሮጀክቱ ሲጠናቀቅ ምን የመስራት ዕቅድ አላችሁ?
ለማህበረሰቡ ሊጠቅሙ የሚችሉ ነገሮችን መስራት፣ የአስተሳሰብ ለውጥ እንዲያመጡ ማገዝ፣ ሴቶችን ማስተማርና መደገፍ እንደሚገባና ይህም ዓለማችንን በመቀየር ረገድ ያለው አስተዋፅኦ ቀላል እንዳልሆነ እናስተምራለን፡፡ አንድ እናት ሳትማር ፕሮፌሰርና ዶክተር ሊሆኑ የሚችሉ ልጆችን ማፍራት ከቻለች፣ ብትማርማ ምን ልትፈጥር እንደምትችል እንሰብካለን፡፡ ከዚህ በኋላ ምንም አያቆመንም፡፡ አብረናቸው ከሰራናቸው ሰዎች የተማርነው የስራ ዲሲፒሊን ቀላል ነገር አይደለም፡፡ በደንብ ቀርፆናል፡፡ ከእነዚህ ሰዎች ጋር ስንሰራ ቆይተን፣ ወጥተን የማይረባ ነገር ለመስራት አንችልም፡፡ ስለዚህም የፕሮጀክቱ መጠናቀቅ አሁን ካለንበት አስተሳሰብና አመለካከት አይለውጠንም፡፡ የህብረተሰባችን አመለካከት ተለውጦ፣ ሴት ልጆች ተምረው የተሻለ ደረጃ ላይ መድረስ የሚችሉበትን ጊዜ ለማየት እጅግ እንናፍቃለን፡፡

Published in ህብረተሰብ
Saturday, 02 May 2015 10:39

የፖለቲካ ጥግ

ምርጫ
በአፍሪካና በአውሮፓ
*አል ባሺር ተቃዋሚዎች በሌሉበት በዝረራ አሸነፉ
*የ71 ዓመት ባለጸጋ፤የ26 አመት ሥልጣን

    እምብዛም የማይገርማችሁን አንድ ወሬ ልንገራችሁ፡፡ ለ26 ዓመታት ሱዳንን የገዙት የ71 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ ኡመር ሃሰን አልበሽር፤ሰሞኑን በሱዳን በተካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ 94 በመቶ ድምጽ በማግኘት አሸንፈዋል ተባለ፡፡ ምርጫ የተባለው ወጉ እንዳይቀር ነው እንጂ አልበሽር ለብቻቸው ነው የተወዳደሩት፡፡ ዋና ዋና የአገሪቱ ተቃዋሚዎች ቀደም ብለው ነው ራሳቸውን ከምርጫው ያገለሉት፡፡  ምርጫው ነጻና ፍትሃዊ አልነበረም የሚሉት ተቃዋሚዎቹ፤ ሲቪል ማህበራትና ሚዲያው በመንግስት ታፍነው እንደነበር ይናገራሉ፡፡ በነገራችን ላይ አልበሽር በ1989 ዓ.ም በመፈንቅለ መንግስት ሥልጣን ላይ ከወጡ በኋላ ይኸው ለ26 ዓመታት ሱዳንን ሲገዙ ቆይተዋል፡፡ አልበሽር በዓለም አቀፉ የጦር ፍ/ቤት የዘር ማጥፋት እንዲፈጸም በማዘዝ ተከሰው በተገኙበት እንዲያዙ ውሳኔ ተላልፎባቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን ዕድሜ ለአፍሪካ ህብረት! ያለመከሰስ ሬዚዳንታዊ መብት አላቸው በሚል የፍርድ ቤቱን አንቀበልም ብሏል፡፡ የሱዳንን ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የአፍሪካ ህብረት ታዛቢ ቡድን የታዘበው ሲሆን አውሮፓ ህብረት፣ አሜሪካ፣እንግሊዝ፣ኖርዌይ ምርጫውን ተችተውታል፡፡ ከወዳጆቿ ጋር በኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ካልሆነ በቀር በፖለቲካዊ ጉዳዮች “ጾመኛ” የሆነችው የቻይና ፕሬዚዳንት በበኩላቸው፤ ለአልበሽር የእንኳን ደስ አልዎ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡አሁንም ከምርጫ አልወጣንም፡፡ ቦታው ግን አውሮፓ ነው፡፡ ጊዜው ደግሞ የዛሬ 12 ዓመት፡፡ የኖርዌይ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር ጄንስ ስቶልትንበርግ፤ራሳቸውን ለምርጫ ውድድር እያዘጋጁ ነበር- ለሦስተኛ ጊዜ አገራቸውን በጠ/ሚኒስትርነት ለመምራት፡፡ ከአገሪቱ ንጉስ ጋር መደበኛውን የአርብ ስብሰባ ከተሰበሰቡ በኋላ አንድ ለየት ያለ ነገር ልሞክር ብለው አሰቡ - ስቶልትንበርግ፡፡ (ማንም ሞክሮት የማያውቅ!) ምርጫ እየደረሰ ስለነበር ጠ/ሚኒስትሩ የድምጽ ሰጪውን ትክክለኛ የልብ ትርታ ለማወቅ ነበር የፈለጉት፡፡ ይሄን የት እንደሚያገኙት ደግሞ ያውቃሉ፡፡ ታክሲ ውስጥ! እናሳ? “እንደ ጠቅላይ ሚኒስትርነቴ የሰዎችን አስተያየት መስማት ይጠቅመኛል፤ ሰዎች የልባቸውን የሚናገሩበት ቦታ ቢኖር ደግሞ ታክሲ ውስጥ ነው” ብለዋል ጠ/ሚኒስትሩ፤ በወቅቱ ለጋዜጠኞች በሰጡት ቃለምልልስ፡፡ ም ኖርዌይን ሁለት ጊዜ በጠ/ሚኒስትርነት ያገለገሉት ስቶልትንበርግ፤ የኦስሎ ታክሲ ነጂዎችን ዩኒፎርም ለበሱና የፀሃይ መነፅራቸውን ሰክተው ታክሲ መሾፈር ጀመሩ፡፡ ጠ/ሚኒስትሩ ለአንድ ተሲያት በኋላ የከተማዋን ነዋሪዎች እያሳፈሩ አገልግሎት ሰጡ - እግረመንገዳቸውንም አስተያየት እያደመጡ፡፡ ከታክሲ ተሳፋሪዎቹ መካከል አንደኛዋ፤ “በዚህ በኩል በጣም ነው ስቶልትንበርግን የምትመስለው” ብላቸዋለች ጠ/ሚኒስትሩን ሹፌር፡፡ ሌላኛዋ ተሳፋሪ ደግሞ ደብዳቤ ልትልክላቸው ትፈልግ እንደነበር ጠቁማ እሳቸውን ታክሲ ውስጥ በማግኘቷ ዕድለኛነቷን ገልፃለች፡፡
ተሳፋሪዎች ከሹፌሩ ጋር የሚያደርጉት ጭውውት በአብዛኛው ወደ ፖለቲካ ያደላ ነበር፡፡ ሚ/ር ስቶልትንበርግ ከአንድ ተሳፋሪ ጋር በትምህርት ጉዳይ ላይ አውርተዋል፡፡ “ዋናው ነጥብ ጎበዝ ተማሪዎች የሚያልሙት ነገር መኖሩን ማረጋገጥና ለሚፍጨረጨሩት ደግሞ  ተጨማሪ እገዛ ማድረግ ነው” ሲሉ ጠ/ሚኒስትሩ ለተሳፋሪው ነግረውታል፡፡ ሰውየው በኦስሎ ታዋቂ ነበሩ፡፡ በዚህም የተነሳ ኋላ መመልከቻ መስተዋት በማየት ብቻ ያወቋቸው ተሳፋሪዎች ነበሩ፡፡ ሰዎች እስካላወቋቸው ድረስ ግን ማንነታቸውን አይገልጹም ነበር፡፡ እናም… የመራጩን ህዝባቸውን እውነተኛ ስሜት … ሃሳብ … እይታ የቻሉትን ያህል ተገነዘቡ፡፡ በእርግጥ ጠ/ሚኒስትሩ በምርጫው አላሸነፉም፡፡ ቁምነገሩ ግን እሱ አይደለም፡፡ ለሚመሩት ህዝብ ያላቸው   አመለካከት ነው፡፡ የአፍሪካ መሪዎች የመራጩን ህዝብ እውነተኛ ስሜት ለመረዳት --- ለማወቅ የሚጨነቁ ይመስላችኋል? (አረ ሲያልፍም አይነካቸው!) እነሱም ግን ምርጫ ሲደርስ አንድ ለየት ያለ ነገር ያደርጋሉ፡፡ (ታክሲ ባይነዱም!) ህገ
መንግስት በመደለዝ የስልጣን ዕድሜያቸውን ያራዝማሉ፡፡ (ሰው እንደየተሰጥኦው ነው!) የአፍሪካ መሪዎች ከማንም በላይ ሥልጣንን ቢወዷትም በቀጥታ ከህዝብ አይደለም የሚወስዷት፡፡ ሲመቻቸው ይነጥቃሉ፡፡ ያጭበረብራሉ፡፡ ራሳቸው ያወጡትን ህግና ህገመንግስት እስከመደለዝ ሁሉ ይደርሳሉ፡፡ የታክሲ ሹፌር ሆኖ የህዝብን የልብ ትርታ ማዳመጥ?--- የሚለውን ግን እርሱት!በነገራችን ላይ በቡሩንዲ ከወር በኋላ በሰኔ አጋማሽ ላይ ሊካሄድ በታሰበው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ወቅት ሊቀሰቀስ ይችላል ብለው ያሰቡትን ብጥብጥ በመስጋት፣ 17 ሺ ቡሩንዲያውያን ከመጋቢት አጋማሽ ጀምሮ ወደ ጎረቤት አገራት (ሩዋንዳና የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ) እንደተሰደዱ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ጠቁሟል፡፡ (በአፍሪካ ምርጫ ያሰድዳል!) የፈሩት አልቀረም፡፡ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ፒሬ ንኩሪኒዛ ፤ህገመንግስቱ ከሚፈቅደው ውጭ ለሶስተኛ ዙር ሊወዳደሩ
መዘጋጀታቸውን ተከትሎ ባለፈው እሁድ ተቃውሞ የገጠማቸው ሲሆን ፖሊስ ሰልፉ ህገወጥ ነው (ህገወጥ እኮ ፕሬዚዳንቱ ናቸው!) በሚል ከሰልፈኛ ጋር በፈጠረው ግጭት፣ ሁለት የተቃዋሚ ሰልፈኞችን የገደለ ሲሆን አራት እንደቆሰሉ የቡሩንዲ ቀይ መስቀል ማህበር ቃል አቀባይ አሌክሲስ ማኒራኪዛ ለሮይተርስ ተናግረዋል፡
በነገራችን ላይ የአፍሪካ መሪዎችና ምዕራባውያን ረብሻና ጠብ ይፈጠራል በሚል የቡሩንዲው ሬዚዳንት በምርጫው እንዳይወዳደሩ አሳስበዋቸው ነበር (“ሚስትህ ወለደች ወይ ቢሉት ማንን ወንድ ብላ” አለ አበሻ!) አሜሪካና አውሮፓም የሳቸውን ወደ ምርጫ መግባት ተከትሎ ብጥብጥ ቢነሳ እርምጃ እንደሚወስዱ ጠቁመዋል (የሰማቸው የለም እንጂ!) አያችሁልኝ አይደል … የአፍሪካን ነገር! አንድ አምባገነን በስልጣን እንዲቀጥል ሺዎች የሚገደሉባት ከንቱ  አህጉር ናት፡፡ እኔ የምለው …. ይሄ አፍሪካ ህብረት የሚባል ድርጅት ውስጡ ሰው የለም እንዴ?! (የቻይና ህንፃ ብቻ እኮ ነው የሚመስለው!)  

   ከዕለታት አንድ ቀን አያ ጅቦ አራት ልጆቹን፤ ማለትም - መዝሩጥን፣ ማንሾሊላን፣ ድብልብልን እና ጣፊጦን ይዞ በለሊት መንገድ ይሄዳል፡፡ እየተጓዙ ሳለ ድንገት አንዲት ከቤቷ የወጣች አህያ ያገኛሉ፡፡
ይሄኔ አባት ጅብ፤
“ልጆቼ ሆይ! እንግዲህ እኔ በጣም አርጅቻለሁና ይቺን አህያ እኔ ነኝ የምበላት! እናንተ ራቅ ራቅ ብላችሁ ትጠብቁኛላችሁ” አለ፡፡
ይሄኔ መዝሩጥ፤
“አባዬ ኧረ አንድ ብልት እንኳን አጋራን?” ይለዋል፡፡
“አይሆንም! ምንም አላቀምስህም” ይላል ጅቦ፡፡
ይሄኔ ማንሾላ ይነሳና፤
“ለእኔስ አባቴ?” ይላል፡፡ አያ ጅቦም፤ “እንካ ጆሮዋን ብላው” ይለዋል፡፡
ቀጥሎ ድብልብል ይመጣና፤
“ለእኔስ አባቴ?” ይለዋል፡፡
“አንተ ሽሆና ይደርስሃል” ይላል አያ ጅቦ፡፡
ቀጠለና ጣፊጦ ጠየቀ፡-
“አባዬ የእኔንስ ነገር ምን አሰብክ?” አለ፡፡
“አንተ ቆዳዋን ካገኘህ ያጠግብሃል” አለ፡፡
ልጆቹ አባታቸው አህያዋን ዘርጥጦ ጥሎ ሲበላ ዘወር አሉ፡፡
አያ ጅቦ ዋና ዋናውን የአህያዋን ብልት እንደበላ፤ ድንገት የአህያዋ ጌታ ሲሮጥ መጣ፡፡
አያ ጅቦ ፈርጥጦ መውጫ የሌለው የጫካ ጥግ ውስጥ ገብቶ ይሰረነቅና እየጮኸ ልጆቹን ይጠራል፡፡ ልጆቹ ቀርበው ወደጫካው ይጠጉና፤
“አባታችን ምነው ትጮሃለህ?” ሲሉ ይጠይቁታል፡፡
አያ ጅቦም፤
“አድነን ልጄ መዝሩጥ?” ይላል፡-
መዝሩጥም፤
“አባቴ ምን ሰጥተኸኛል እንደበላህ እሩጥ!” ይለዋል፡፡
“አድነኝ ልጄ ማንሾለላ!” ይላል አያ ጅቦ፡፡
“ምን ሰጥተኸኛል ካንድ ጆሮ ሌላ!?” ይለዋል ማንሾለላ፡፡
“አድነኝ ልጄ ድብልብል?”
“አይ አባት! ሸሆና ለማን ውለታ ይሆናል?!”
ቀጥሎ አያ ጅቦ ጣፊጦን ጠየቀ፤
“አድነኝ ልጄ ጣፊጦ?!”
“ማን የጎረሰውን ማን አላምጦ?” አለ ጣፊጦ፡፡
መላወሻም አጋዥም ያጣው አያ ጅቦ፤ እዚያው ተወጋና ሞተ፡፡
*           *          *
ዛሬ  እኔ ነኝ ዋናው ጅብ ማለት አይሠራም! ቀድመው ያላሰቡበት ግለኝነትና ሆዳምነት ምን ላይ እንደሚጥለን አለማሰብ የማታ ማታ ያላጋዥ ያለመጠጊያ ያስቀራል፡፡ ከካፒታሊዝም ምርኮኛነታችን ጀምሮ ስግብግብነት፣ በዝባዥነት፣ ዘረፋና ግፍ ይበረክታል፡፡ ያላየነው የገንዘብ ትርፍ ማህበራዊ መልካችንን ያዥጎረጉረዋል፡፡ እንኳን ሊያተርፈን ራሳችንን ያጎልብናል፡፡ “አድነኝ ልጄ እገሌ?” ቢባል ምላሽ አይኖረውም፡፡ ዛሬ ከመቼውም ጊዜ በላይ እርስ በርስ መግባባትና መስማማት ያለብን ሰዓት ነው፡፡ የሃይማኖት መግባባታችን፣ ስለአንድነት መግባባታችን፣ ስለድንበር ጉዳይ መግባባታችን፤ ስለዓለም አቀፍ እንቅስቃሴዎች መግባባታችን፤ ከሁሉም በላይ ስለአይኤስአይኤስ መግባባታችን… ብርቱ ጥረት ማድረግን የሚጠይቅ ዘመን ነው፡፡ የሳሱ ድንበሮችና መንግስት አልባ አገራት ወደ አሰቃቂ እልቂት ሊያመሩ እንደሚችሉ፤ ሶማሊያም፣ የመንም፣ ሊቢያም፣ ኢራቅም ለመነሻ አስረጅነት የቆሙ ተጨባጭ ምሳሌዎቻችን ናቸው! ነገ በየአገሩ ይሄው ሁኔታ ላለመከሰቱ ምንም አስተማማኝ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ህልውና የለም፡፡ በትናንሽ የፖለቲካ አታካራ ተሞልተን፣ ትናንሽ ሙሾ በማውረድ ጊዜያችንን ከምናባክን፣ ትልቁን የዓለም አቀፍም አገር አቀፍም ስዕል (The Bigger Picture) የምናይበትን ዐይናችንን እንክፈት፡፡ ምዕራባውያን፤ ባህል፣ ሃይማኖት እና ጥናታዊ ታሪክ ያላቸውን አገሮች ኢራቅ፣ ኢራን፣ ሶርያ፣ የመን፣ ግብፅ፣ ህንድ፣ ጃፓን፣ ቻይና … አሁን ደግሞ የእኛው አገር ኢትዮጵያ ላይ ያነጣጠሩት ያለነገር አይደለም፡፡ ግሎባላይዜሽንን ይነቅፋሉ የሚለው አጀንዳ የዋዛ አይደለም፡፡ ባህል የሌላቸው ባለባህሎቹን እየገደሉ ነው፡፡ የቅርቦቹ ሶማሊያና ሊቢያ በመንግሥት-አልባ ሁኔታ ውስጥ መሆን፣ በማንም ይሁን በማን ለመጠቃታቸው ሰፊ በር ከፍቷል፡፡
ወደ ሊቢያ በጣሊያን አዛዥነት ስለዘመተው ያለዕዳው ዘማች የኤርትራ ወጣት (ደራሲው አበሻ ይለዋል) እንዲህ የሚል ሀሳብ ይገኝበታል፡፡ ስለሊቢያ በረሀ ነው፡-
“የመሸበር ስሜት፣ ሐዘን፣ ተስፋ ቢስነት እና ፀፀት ፊታቸው ላይ ይነበባል፡፡ የበረሀው ስዕል አሰቃቂ ነው፡፡ አንዲት ዛፍ አትታይም፡፡ አንዲትም የሳር አገዳ የለችም፡፡ የውሃ ነገርማ ባይነሳ ይሻለዋል፡፡ ወደየትም አቅጣጫ መንቀሳቀስ አይታሰብም፡፡ ግራ፣ ቀኝ፣ ወደ ፊት፣ ወደ ኋላ፣ ወደየትም መሄድ አይቻልም ምክንያቱም የትም ይሁን የት ህይወት በአሸዋ ተከባ ነው የምትገኘው፡፡ በየትም ቢዞሩ ጠጠር ኮረት ድንጋይ፣ እና የአቧራ ክምር!
ያ በረሀ እንደባህር ሰፊ፣ ግን በጥላቻ የተሞላ!  ባህሩ ውስጥ ቢያንስ ዓሣ ማየትና የማዕበል ድምፅ ማዳመጥ ይቻላል፡፡ እዚህ ሊቢያ በረሃ ግን አንዲትም ወፍ አትዘምርም፡፡ አትበርምም፡፡ ያ ክፍቱ ደመና አልባ ሰማይ የጋለ ምድጃ ነው፡፡ በዚያ ጠራራ ንደድ ውስጥ ያለ ሰው፣ ያ መሬት፣ የህይወት ይሁን የሞት መለየት ይሳነዋል፡፡ ይሄን መሬት ከአረንጓዴው፣ ከንፋሳማው እና ከለሙ የኢትዮጵያ ምድር ጋር ማነፃፀር ከንቱ ድካም ነው! የሲዖልና የገነት ነው ልዩነቱ!?”
ስለአበሻ የጦርነት ብቃት የሚገርም ትንተናም አለው - በሊቢያ በረሐ፡- አበሻ፣ ጣሊያንና አረብ የውጊያ መንፈሳቸው ምን ይመስላል?
“ለአበሻ፣ ጦርነት ውጤቱ ምንም ዋጋ ያስከፍል ወደፊት መግፋት ነው፡፡ (ግፋ በለው እንደማለት) ለጣሊያኖች፤ አዛዥህ እንዳለህ ተዋጋ ነው፡፡ ጠላት ግንባር ለግንባር ቢፋጠጥህም ካልታዘዝክ አትተኩስም፡፡ ካልታዘዝክ ብትታረድም ፀጥ በል ነው!
ለዐረቦች ወደ ጠላትህ ፈጥነህ ሩጥ፡፡ ሁኔታው የሚያዋጣ ከመሰለህ ነብስህን ለማዳን ፈርጥጥ ነው፡፡ የየተዋጊውን ባህሪ ለእኔ ብሎ መስማት የእኛ ፈንታ ነው፡፡ ጊዜው አስጊ ነው፡፡ ጎረቤቶቻችንን በቅጡ እናስተውል፡፡ ሩቅ የሚመስሉንን ዕጣ ፈንታ ስናይ፣ “ያንተ ቤት ሲንኳኳ ይሰማል እኔ ቤት!” እንበል፡፡ “ጎረቤትክን ሲያማ ለእኔ ብለህ ስማ!” ማለት የአባት ነው!! 

Published in ርዕሰ አንቀፅ

      መንግስት አለማቀፍ ህገ ወጥ ሰው አዘዋዋሪ ደላላዎችን ለመቅጣት የሚያስችል አዲስ ህግ እያረቀቀ መሆኑን ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ህገ ወጥ የሰዎች ዝውውር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ በመሆኑ በእንቅስቃሴ የሚሳተፉ አካላትን ከወንጀለኛ መቅጫ ህጉ በተሻለ የሚያስቀጣ የህግ ረቂቅ በፍትህ ሚኒስቴር ተዘጋጅቶ በቅርቡ ይጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
“ህጉን ማውጣት ያስፈለገው በድርጊቱ የሚሳተፉ አካላትን እስካሁን በማስቀጣት የሚወሰዱት እርምጃዎች አርኪ ባለመሆናቸው ነው” ያሉት የፍትህ ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው አምባዬ፤ “ህገ ወጥ የሰው አዘዋዋሪ ደላላዎች ለኢትዮጵያውያን ስደት መባባስ ተጠያቂዎች ናቸው” ብለዋል፡፡
አሁን በስራ ላይ ያለው ህግ በዚህ ወንጀል ተሳታፊ የሆኑ ግለሰቦችን እስከ 20 ከመቶ እስራት የሚያስቀጣ ሲሆን አዲስ የሚረቀቀው ህግ የተሻሉ የቅጣት እርከኖች ይኖሩታል ተብሎ እንደሚጠበቅ አቶ ጌታቸው ገልጸዋል፡፡
በቅርቡ በሊቢያ አይኤስ (ዳኢሽ) የተሰኘው የሽብር ቡድን 30 ኢትዮጵያውያን ስደተኞችን በአሰቃቂ ሁኔታ መግደሉን ተከትሎ መንግስት በዋናነት ህገ ወጥ ደላሎችን ተጠያቂ ያደረገ ሲሆን እርምጃ እንደሚወስድም መግለፁ ይታወሳል፡፡

Published in ዜና