የማይመለሱ 4 ነገሮች፡- ከአፍ የወጣ ቃል፣ የተወረወረ ቀስት፣ ያለፈ ህይወት እና የባከነ ዕድል፡፡
የቻይናውያን አባባል
ለማቀድ መስነፍ ለመውደቅ ማቀድ ነው፡፡
የቻይናውያን አባባል
ማለም ብቻ በቂ አይደለም፤ መምታት አለብህ፡፡
የጣሊያኖች አባባል
መሬት ላይ እሾህ ከበተንክ ባዶ እግርህን አትሂድ፡፡
የጣሊያኖች አባባል
ሁልጊዜ የምትሰጥ ከሆነ ሁልጊዜ ይኖርሃል፡፡
የቻይናውያን አባባል
በአንድ እጅህ ሁለት እንቁራሪቶችን ለመያዝ አትሞክር፡፡
የቻይናውያን አባባል
የተጠበሰች ዳክዬ መብረር አትችልም፡፡
የቻይናውያን አባባል
አበቦች በያዛቸው እጅ ላይ መዓዛቸውን ይተዋሉ፡፡
የቻይናውያን አባባል
ጠብ ከፈለግህ ለጓደኛህ ገንዘብ አበድረው፡፡
የቻይናውያን አባባል
የምላስ ብዕር፣ የልብ ቀለም ውስጥ መነከር አለበት፡፡
የቻይናውያን አባባል
የአንድ ዓመት ብልጽግና ከፈለግህ እህል ዝራ፤ የ10 ዓመት ብልጽግና ከፈለግህ ዛፎች ትከል፤ የ100 ዓመት ብልጽግና ከፈለግህ ሰዎችን አልማ፡፡
የቻይናው ያን አባባል
የአንድ ሰዓት ደስታ ከፈለግህ አሸልብ፤ የአንድ ቀን ደስታ ከፈለግህ ሃብት ውረስ፤ የዕድሜ ልክ ደስታ ከፈለግህ ሰዎችን እርዳ፡፡
የቻይናውያን አባባል

Published in ከአለም ዙሪያ

ወይዘሮ ተናኘ ስዩም “የፍቅር ድንግልና” በሚል ርዕስ ፅፈው ያሳተሙት ረጅም ልብወለድ መፅሃፍ በዛሬው ዕለት ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ በአምስት ኪሎ ድህረ ምረቃ አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በምረቃ ስነ - ስርዓቱ ላይ ደራሲ አበረ አዳሙ በመፅሃፉ ላይ ሥነ - ፅሁፋዊ ዳሰሳ ያቀርባል ተብሏል፡፡
ደራሲዋ የዕውቋ ድምፃዊት ጂጂ (እጅጋየሁ ሽባባው) እናት እንደሆኑ ታውቋል፡፡ የልቦለዱ ታሪክ ከኢጣሊያ ወረራ በፊትና በኋላ የነበረች አንዲት ወጣት ላይ የሚያጠነጥን ሲሆን የወቅቱን ባህላዊና ማህበራዊ ገፅታ ያሳያል። በ349 ገፆች የተቀነበበው “የፍቅር ድንግልና”፤ በ100 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ 

የወጣት ፍሬዘር ዘውዴን (ቬኛ) የግጥሞችና ደብዳቤዎች ስብስብ የያዘው “የፍቅር ገፆች” የተሰኘ መድበል ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ለንባብ በቅቷል፡፡
መፅሃፉ በ110 ገፆች 52 ግጥሞችንና 12 ደብዳቤዎችን ያካተተ ሲሆን ለአገር ውስጥ በ30 ብር፣ ለውጭ አገራት በ9.99 ዶላር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡

በአለማየሁ ገበየሁ የተፃፈው  “የረከሰ ፍርድ በኢትዮጵያ” የተሰኘ የአጫጭር ወጐች መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡
ጭብጡን ፖለቲካዊና ማህበራዊ ጉዳዮች ላይ ያደረገው መጽሐፉ፤ ታሪኮቹ በወግ መልክ  የቀረቡ ናቸው፡፡ ደራሲ አለማየሁ ገበየሁ የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅትን ጨምሮ በተለያዩ ሚዲያዎች በጋዜጠኝነት መስራቱ ታውቋል፡፡
ደራሲው በእለት ማስታወሻ ደብተሩ የመዘገባቸውን አስገራሚ ሁነቶች በወግ መልክ ማቅረቡን  የጠቆመ ሲሆን መፅሃፉ በ49 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

  ከ1.5 ሚ. ብር በላይ ፈጅቷል

   የጠፈር ሳይንስ ተመራማሪ የነበሩትን የሳይንቲስት ዶ/ር ቅጣው እጅጉ ህይወት የሚዳስስ የ50 ደቂቃ ዘጋቢ ፊልም በዛሬው ዕለት ከምሽቱ 12፡30 ጀምሮ በሂልተን ሆቴል ይመረቃል፡፡
“ልጃችን” የተሰኘውንና ከ1.5 ሚ. ብር በላይ ወጪ የተደረገበትን ይሄን ዘጋቢ ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ ከ2 ዓመት በላይ እንደፈጀ የዶ/ር ቅጣው እጅጉ ቤተሰቦች ጠቁመዋል፡፡ ከቦንጋ እስከ አሜሪካ ድረስ ያለውን የሳይንቲስቱን ህይወት በስፋት ይዳስሳል በተባለለት በዚህ ዘጋቢ ፊልም፤ ከዶ/ር ቅጣው ጋር ተያይዘው የሚነሱ በርካታ የተዛቡ ጉዳዮች ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል ተብሏል፡፡

 ባለፈው ዓመት በአገራችን ለመጀመሪያ ጊዜ በብሔራዊ ቴአትር የተከበረው “የዓለም የቴአትር ቀን”፤ በደሴ ከተማና በኮምበልቻ እንደሚከበር በባህልና ቱሪዝም ሚ/ር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር አስታወቀ፡፡
“ቴአትር ለማህበራዊ ለውጥ፤ ማህበራዊ ለውጥ ለቴአትር” በሚል መሪ ቃል ከዛሬ ጀምሮ ለ3 ቀናት የሚከበረውን በዓል ወሎ ዩኒቨርሲቲና የባህልና ትብብር ዳይሬክቶሬት በጋራ እንዳዘጋጁት ታውቋል፡፡
“የዓለም የቴአትር ቀን” በደሴና ኮምበልቻ በተለያዩ አዳራሾች እንደሚከበር የጠቆሙት አዘጋጆቹ፤ በየመድረኩ ቴአትሮች፣ ትውፊታዊ ድራማዎች፣ ልዩ የሙዚቃ ዝግጅቶችና ቱባ ባህልን የሚያንፀባርቁ ውዝዋዜዎች፣ የቅኔ ጉባኤ፣ መንዙማና ሌሎች ኪነ - ጥበባት ይቀርባሉ ብለዋል፡፡
“የዓለም የቴአትር ቀን” ከ1962 ዓ.ም አንስቶ በዓለም አቀፍ ደረጃ መከበር የጀመረ ሲሆን ዘንድሮ ለ53ኛ ጊዜ እንደተከበረ ተጠቁሟል፡፡

የደራሲ ተስፋዬ ዘርፉ “የስደታችን ማስታወሻ” የተሰኘው መፅሃፍ በነገው ዕለት ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ውይይት እንደሚካሄድበት ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ገለፀ፡፡ ለውይይቱ መነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፕሬስ ኤዲተር የሆኑት አቶ ብርሃኑ ደቦጭ ሲሆኑ ውይይቱ በብሔራዊ ቤተ - መፃህፍትና ቤተ - መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ እንደሚካሄድ ታውቋል፡፡ የሥነ - ፅሑፍ አፍቃሪያን በውይይቱ ላይ እንዲገኙ ሚዩዚክ ሜይዴይ ጥሪ ጋብዟል፡፡

Saturday, 06 June 2015 14:23

የዕብደት ዋዜማ

 “ተራሮች ጫፍ ላይ ጸጥታ ሰፍኗል”  ዛፎች ሁሉ ረጭ ብለዋል፡፡ አዕዋፍ በዛፎቹ ላይ አሸልበዋል - ጠብቅ! አንተም አንድ ቀን እንዲህ ጸጥ ትላለህ!!!” የሚል የት እንዳነበብኩት የማላስታውሰው ጥቅስ በተደጋጋሚ በእዝነ ህሊናዬ አስተጋባ፡፡
“ጸጥ ትላለህ” ምን ማለት ነው?
በዚህ ስገረም ይባስ ብሎ፣ ከእንቅልፌ በነቃሁበት ቅጽበት “ዛሬ ትሞታለህ” የሚል ጥርት ያለ ድምጽ በጆሮዬ ሰማሁ፡፡ ማነው ሹክ ያለኝ? ሰይጣን ወይስ መላእክት? የዕብደት ዋዜማ ላይ ነኝ ልበል፡፡
ስለ አይቀሬው ጥቁር እንግዳዬ ሞት ማውጠንጠን ጀመርኩ…፡፡ ሞት!!
የሞት መንገደኞች ነን፡፡ ዝንተ ዓለም የሰው ልጅ የተመላለሰበት ማለቂያ የሌለው መንገድ፡፡ ወትሮም መንገደኛ ፊትና ኋላ ነው እንዲሉ… ሞት የተራ ጉዳይ ነው፡፡ መንትዮች እንኳን ተራ በተራ አይደል የሚወለዱት! የባለ ቅኔው ጆን ዶን ግጥም ትዝ አለኝ….
No man is Island entire of it self
Every man is a piece of continent
A part of the main
And therefore never sent to know
For whom the bell tolls….
ቀጣዩ ደወል የሚደውለው ለማን ነው? የሞት ደወል የሚደወለው ….
“ላንተ! ላንተ ነዋ!”… ጥርት ባለ ድምጽ አይምሮዬ ላይ አቃጨለ፡፡ ተርበተበትኩ፡፡ የመኖር ጥማት ውስጤ ተላወሰ፡፡ ህይወት፡፡… ህይወትማ በምድር ላይ ለሚታይ ትርኢት የመግቢያ ትኬት ናት። ትርኢቱን በቀጥታ ስርጭት እነ አልጄዚራ፣ ሲኤንኤን…ፕሬስ ቲቪ በየደቂቃው ያሳዩናል፡፡ ምድር ዛሬ ተነስቶ ሲያንቀጠቅጣት - ሆድ ብሷት እሳተ ጎመራዋን ስታስመልስ -  እንደጧፍ ቦግ ብላ ስትነድ።….
እንደ ምጽአት ቀን ውርጅብኝ ሁሉም ነገር ሲደበላለቅ! ብው! ድም!  ዶግ አመድ! ወይ ዓለም! - የራሷ ጉዳይ ድራሽ አባቷ ይጥፋ!! …. የዕብደት ዋዜማ ላይ ነኝ ልበል፡፡ እንዲህ ቦግና ዕልም፣ ብልጭና ድርግም የሚሉ አሳቦች ጭንቅላቴ ውስጥ መፈንዳት ጀመሩ፡፡ ለማንኛውም የዛሬው ውሎዬ ህይወቴን ለማዳን በሚደረግ ጥንቃቄ ያልፋል፡፡
ከቤት መውጣት የለብኝም - በየመንገዱ በሀሳብ ስናውዝ አንዱ ከላባ ሲኖትራከር ቢጨልቀኝስ? ከዚህ ሁሉ ቤት መሰብሰቡ ይሻላል። ክፍሌ አስተማማኝ ናት ደራሲውን በድንገተኛ ርዕደ መሬት ዶግ አመድ ካልሆነች …. አልያም መብረቅ ወርዶ ሁለት ቦታ ካልተሰነጠቀች በቀር በቤቴ ውስጥ ለህይወቴ የሚያሰጋኝ አንዳች ነገር የለም፡፡ አልጋዬ ላይ ተጋደምኩ፡፡ የተገረዝኩበት አልጋ ነው፡፡ በዛሬው እለት ይህችን ምድር የምሰናበት ከሆነም እገነዝበት ይሆናል፡፡ “በተገረዝክበት አልጋ ትገነዝበታለህ” የሚለው በኔ ይደርስ ይሆን፡፡ የሩሲያ ደራሲውን የሚካኤል ሌርሞንቶቭ ልብወለድ ማንበብ ጀመርኩ… አንዱ ገጸ ባህሪ … “በአንድ ውብ ማለዳ በሞት እለያለሁ፤ ምክንያቱም በአንድ በተረገመ ሌሊት ወደዚህ ዓለም በመምጣቴ ….”
የራሴ ህልፈት ትዝ ብሎኝ መጽሐፉን ዘጋሁት። ምን ማለቱ ነው? የተረገመ ሌሊት… የተወለደበት ወይስ የተጸነሰበት?
ቀኑን ሙሉ “ሞት ሆይ መውጊያህ የታል” በሚል ስቁለጨለጭ ዋልኩ ….
ከምሽቱ 2፡00 ሰዓት ወጣ በል፤ ትንሽ ቀማምስ የሚል ሀሳብ መጣልኝ፡፡ አንድ ሁለት ብዬ መለስ ብልስ -ብዙም ሳርቅ፡፡ ቡና ቤት ገባሁ - ወደ ፈንጅ ወረዳ! በሰላም እወጣ ይሆን ከነሕይወቴ፡፡ ድራፍት አዘዝኩ፡፡ ላጥ አድርጌ ሌላ ደገምኩ… ጆሮዬ ድምጽ መስማት ጀመረ …
“የህልም እንጀራህን እዛው”
“የህልም እንጀራህን ብሎ ነገር የለም - በህልም አብሲት ሳይጣል …”
“ለሚቀጥለው ምርጫ መቀናጀት ብቻ ሳይሆን - መቆራኘት ነው - ለምርጫ 2017”
“ለምርጫ 2017 ወይስ 2077 … ኢሂሂ … ቂቂቂ….”
እያለ የሚገለፍጠው ላይ አይኔ አረፈ፡፡ እዚህ ቤት ሳምንት ሙሉ አይጠፋም፡፡ የአንዳንድ ሰው ሳምንት ሰባት ቅዳሜዎችን የያዘ ነው ልበል፡፡ ሁሌም ከበር ቻቻ፡፡
“የቡና ቤቷ ባለቤት እየተንጎማለሉ ገቡ፡፡ ወደኔ እያመለከቱ ለአስተናጋጁ የሆነ ነገር ሹክ አሉት፡፡
‹ለምን ለዚህ ቀውስ  ወፈፌ ቀዳህለት” እንደሚሉት እርግጠኛ ነበርኩ …
“ድራፍት” ስል አዘዝኩ፡፡
“የለም” ሲል መለሰልኝ፡፡
ውስጤ ተናወጠ፡፡ እልህ ያዘኝ፡፡ ብርጭቆ ላይ የቀረውን ጭላጭ ድራፍት አስተናጋጁ ፊት ላይ ደፋሁበት፡፡ የድራፍቱን ብርጭቆ ከጭንቅላቴ ጋር ቴስታ አጋጠመው … ተፈተንኩ … ቢሆንም ለሞት የሚያበቃ የከፋ አደጋ አልደረሰብኝም… ብርጭቆውም ሆነ ጭንቅላቴ አንዳቸውም አልተሸረፉም፡፡
ቤት ደረስኩ - ምስሌን ለማየት መስታወቱ ላይ አፈጠጥኩ - የለሁም፡፡ አይኔን በድንጋጤ ጎልጉዬ መስታወቱ ላይ ደገሜ አፈጠጥኩ። የለሁም፡፡ ታዲያ የት አለሁ? በቁሜ አልጋዬ ላይ ወደቅኩ፡፡ ወደ እንቅልፍ ይሁን ወደ ሞት ዓለም በስሱ እየተጓዝኩ ነው፡፡ የሬዲዮ ድምጽ ይሰማኛል፡፡ በእውን ይሁን በሰመመን …. በቅዠት … የጋዜጠኛው ድምጽ ቅድም ቡና ቤት ውስጥ ምርጫ 2017 … 2077 እያለ በፍልጥ ጥርሱ ሲገለፍጥ ከነበረው ድምጽ ጋር ተመሳሳይ ነበረ፡፡
“በምርጫ 2017 በክልል 99 የተወዳደረው ፓርቲ፤ አብላጫ የክልሉን ም/ቤት መቀመጫ በማግኘት ማሸነፉ ይታወቃል፡፡ ይህ በተቃዋሚ ፓርቲ ደረጃ የመጀመሪያው ነው፡፡ የክልል 99 ፕሬዚዳንት የካቢኔ አባላት ሹመትን በተመለከተ FM 99.9 በቀጥታ ያስተላልፍላችኋል … የፕሬዚዳንቱ ሙሉ ቃል እነሆ ….
“… ክቡራን …. ፓርቲያችን አሸንፎ  ለዚህ ድል በመብቃቱ የተሰማኝን ደስታ በመግለፅ… ወደ ሹመት ዲስኩሬ እገባለሁ፡፡ በመጀመሪያ የክልሉ ኢንዱስትሪ ኃላፊ ሹመትን በተመለከተ … በክልላችን የምናገኘው የጎጆ ኢንዱስትሪ ነው። ብቸኛ የጎጆ ኢንዱስቱሪ ተረፈ ምርት የሀበሻ አረቄ ወይም ቁንድፍቱ መሆኗን ሁላችንም የምናውቀው ሀቅ ነው፡፡ ለዚህ ኃላፊነት ይገባኛል የሚል በግል ያነጋግረኝ፡፡ ያለበዚያ በአረቄ ምርት አቅራቢነታቸው በክልሉ ዝናን ያተረፉትን ወ/ሮ ደብሪቱን የምንሾምበት ምክንያት የለም - ስራ ለሰሪው … በመቀጠል የከተማ ልማት ሹመትን አቀርባለሁ … የክልል 99 መዲና እንኮዬ አርጅታ … ዝጋ… የጉስቁልና ሕይወቷን እየገፋች ነው። እንደ መንግስተ ሰማያት በር የጠበቡ መንገዶቿ የትም አይደርሱም፡፡
ጉሮሮዋ ታንቆ የጣር ሕይወት እየገፋች ነው - የቀባሪ ማጣት ካልሆነ በቀር … የተባበሩት መንግስታት ‹ግጭት አስወጋጅ›፣ ‹ድህነት ቅነሳ›…. ኮሚሽኖቹ እንዳሉት ሁሉ የሞቱትን ከተማ ቀባሪ ኮሚሽን ቢኖረው ስል እመኛለሁ … የኛዋ እንኮዬ የዚህ እድል የመጀመሪያ ተጠቃሚ ሆና እፎይ ትል ነበር … ኑሮ ካሉት መቃብር ይሞቃል እያለች … የከተማ ልማት ኃላፊ ሹመት ከላይ የገለጽኩት ያማከለ መሆን አለበት፡፡ ለቦታው የሚጠይቀው መስፈርት ቢበዛ የዕድር ዳኛ፣ ቢያንስ የድር ጥሩንባ ነፊ …. ንግግራችን በሞተችዋ እንኮዬ ላይ በመሆኑ ….
… የክልሉ ሴቶች ጉዳይ ተጠሪን በተመለከተ … እንደሚታውቀው በዚህ ምክር ቤት አንድም እንስት የለችም … ያሳዝናል … ፓርቲያችን ጉሮሯችን እስኪደርቅ - ላንቃችን እስኪሰነጠቅ “ሔዋን ሆይ ለክልል ም/ቤት ተወዳዳሪ” አልን … ግን ማን ሰምቶን? ጩኸታችን እንደ መጥምቁ ዮሐንስ የምድረ በዳ ጩኸት ሆኖ ቀረ … በመሆኑም አንድም እንስት በዚህ ም/ቤት የለችም። ማንን ኃላፊነት ላይ ላስቀምጥ በሚል የአይምሮዬን መዝገብ ሳላገላብጥ ገጽ አንድ ላይ አቶ ማዕረጉን አገኘሁ። ማዕረጉ ከወንዳወንድነቱ ሴታሴትነቱ ያመዝናል፡፡ መቅለስለሱ መሽኮርመሙ፣ ለስላሴ ተፈጥሮው የሄዋንን ውብ ጸጋ ጥዑም ለዛ አላብሶታል፡፡
ተነሳሽነቱ… ጽኑ ፍላጎት ካለው ከክልሉ በጀት ወጪ በማድረግ ፣ ለሙሉ የፆታ ለውጥ ለህክምና ወደ ውጭ ለመላክ ፍላጎቴን በዚህ አጋጣሚ ለመግለጽ እወዳለሁ … በዚህ ንግግሬ አቶ ማዕረጉ ቅር እንደማይለው ዕምነቴ ነው፡፡ ምክንያቱም በልማትና በለውጥ ስለሚያምን - ፆታዊ ለውጥ ቢሆንም

Published in ልብ-ወለድ
Saturday, 06 June 2015 14:21

የፍቅር ጥግ

ፍቅር የሚያንዘፈዝፍ ደስታ ነው፡፡
ካህሊል ጂብራን
እግዚአብሄር የተሰበረ ልብ መጠገን ይችላል፡፡ ነገር ግን ስብርባሪዎቹን ሁሉ ማግኘት አለበት፡፡
ያልታወቀ ደራሲ
የትዳር ግብ ተመሳሳይ ነገር ማሰብ ሳይሆን አብሮ ማሰብ ነው፡፡
ሮበርት ሲ.ዶድስ
ሚስት ጥሩ ባል ሲኖራት ፊቷ ላይ ያስታውቃል፡፡
ገተ
አባት ለልጆቹ ማድረግ የሚችለው ትልቁ ነገር እናታቸውን መውደድ ነው፡፡
ቲዎዶር ሄስበርግ
አንዳንዴ አንድ ሰው ስናጣ መላው ዓለም ህዝብ አልባ የሆነ ይመስለናል፡፡
ላማርቲን
እግዚአብሔር የተሰበረ ልብ ላላቸው ቅርብ ነው፡፡
የአይሁዶች አባባል
ሁልጊዜ ከሚስቴ ጋር እጅ ለእጅ እንያያዛለን። ከለቀቅኋት አንድ ነገር ትገበያለች፡፡
ሄኒ ያንግማን
አብሮ መሆን ጅማሮ ነው፡፡ አብሮ መቀጠል ዕድገት ነው፡፡ አብሮ መስራት ስኬት ነው፡፡
ሔነሪ ፎርድ
በእኔ ቤት ውስጥ አለቃው እኔ ነኝ፤ የሚስቴ ሚና የውሳኔ ሰጪነት ብቻ ነው፡፡
ውዲ አለን
ትዳር ለማደግ የመጨረሻችን ምርጥ አጋጣሚ ነው፡፡
ጆሴፍ ባርዝ
ሃዘን በጊዜ ክንፍ በርሮ ይሄዳል፡፡
ዣን ዲ ላፎንቴን
አንተ በልቤ ክንፍ በርረህ ሄድክ፣ እኔን ግን ክንፍ አልባ አደረግኸኝ፡፡
ቴሪ ጉይሌሜትስ
ትዳርን ጠብቆ የሚያቆየው ሰንሰለት አይደለም፡፡ ክሮች ናቸው፡፡ ሰዎችን በአንድ ላይ ሰፍተው የሚያቆዩት በመቶዎች የሚቆጠሩ ቀጫጭን ክሮች ናቸው፡፡
ሳይሞን ሲኞሬት

Published in የግጥም ጥግ

  አንደኛ ዓመት ልደት!
           
   “በክረምት በሚያገኙት ዝናብ መሬታቸውን እያረሱ በእርሻ የሚተዳደሩ የገጠር ነዋሪዎች! ዝናቡ ጊዜውን ጠብቆ ባለመምጣቱ ብቻ ሳይሆን ሰማዩም ደመና አለመቋጠሩን ሲረዱ ለፈጣሪያቸው እግዚኦታ ሊያቀርቡ ቀጠሮ ተይዞ፣ ሁሉም የአባወራ ቤተሰብ እንዲገኝ ጥሪ ተደረገ፡፡ የሰማ ላልሰማ እየነገረ በቀነ ቀጠሮው ዕለት ብዙ ሕዝብ በአደባባይ ተገኘ፡፡ የሃይማኖት አባቶች ምህላውን ሊያስጀምሩ ሲሉ፣ የጐበዝ አለቃው አንድ ሰው ከሩቅ ሲመጣ አይቶ ሥነ ስርዓቱ እንዲዘገይ አደረገ፡፡
“በሩቅ የታየው ሰው በእጁ ጥቁር ነገር ይዟል፡፡ እየቀረበ ሲመጣ የያዘው ነገር ብቻ ሳይሆን ወደ ምህላው አደባባይ እየመጣ ያለው ሰው በዕድሜውም ልጅ መሆኑ ታወቀ፡፡ ልጁ የያዘው ጥቁር ነገርም ዣንጥላ ነበር… ይህንን ተረት የንግግሬ መጀመሪያ ያደረኩት አንድ ነገር ለመጠየቅም ይሁን ለመጀመር ሲታሰብ፣ ጀማሪነትና ጠያቂነት የሚያስከትለውን ነገር ቀድሞ የመገመት አስፈላጊነትና የተፈለገው ነገር ሲገኝ የሚያመጣውን ጥቅምና ጉዳት ቀድሞ መገመት መቻል ውጤቱን በአዎንታ ለመቀበል ጥሩ ማሳያ ስለሆነ ነው፡፡”
ንግግራቸውን በተረት የጀመሩት የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሙሴ ያዕቆብ ሲሆኑ ዕለቱ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ ግንቦት 22 ነበር፡፡ ቦታው በብሔራዊ ሙዚየም ግቢ በሚገኘው ሉሲ ጋዜቦ ሬስቶራንት አዳራሽ ውስጥ ነው፡፡ ፕሮግራሙ ደግሞ
“የብራና ልጆች የቴሌቪዥን ፕሮግራም” የተመሠረተበትን አንደኛ ዓመት በዓል ተከብሯል፡፡ “የብራና ልጆች ፕሮግራም መተላለፍ ሲጀምር አንዴት ዘላቂ ማድረግ ይችሉ ይሆን የሚል ስጋት ነበረኝ፡፡ ፈጣሪ ምህላቸውን ሰምቶ፣ ዶፉን ቢያወርደውስ ብሎ አርቆ በማሰብ፣ ዣንጥላ ይዞ እንደመጣው ልጅ የብራና ልጆች ፕሮግራም አዘጋጆችም ሲጀምሩ ለቀጣይነቱም ስላሰቡበት አንደኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ለማክበር ችለዋል” በማለት ዶ/ር ሙሴ አድናቆታቸውን ገልፀዋል፡፡
መፃሕፍትን፣ ፀሐፊያንንና ንባብን ማዕከል አድርጐ በኢቢኤስ ቴሌቪዥን የሚተላለፈው “የብራና ልጆች” ፕሮግራም፤ ሥዕልና ሙዚቃን ከርዕሰ ጉዳዩ ጋር በማቅረብ፤ የጥበብን ሕብራዊነትና ተደጋጋፊነትን በተግባር እያሳየ ይገኛል፡፡ በበዓሉ ላይ በአሸናፊ ቻምበር ኦርኬስትራ የታጀቡ ግጥሞች ተነበዋል፡፡ ወጐችና ከመፃሕፍት የተመረጡ አንቀፆችም ቀርበዋል፡፡
በምሽቱ ዝግጅት ለየት ያሉ ትኩረት የሚስቡ ሥነ ስርዓቶችም ነበሩ፡፡ “አያ ቶኔ ቶር” በሚል ርዕስ የቀረበው ሙዚቃዊ ተውኔት አንዱ ነው፡፡ “እናት ኢትዮጵያ” ብዙ ጊዜ በሴት ገፀ ባሕሪ ስትወከል እንመለከታለን፡፡ “አያ ቶኔ ቶር” ጥንታዊ የኢትዮጵያን ዕውቀት ወክሎ ቀርቧል፡፡ ገፀ ባሕሪው “እየጠፋሁ ነው፣ በመዘረፍ አደጋ ውስጥ ነኝ፣ የመረሳት ችግር ገጥሞኛል፣ አድኑኝ!” በሚል ላቀረበው ጥሪ፤ በአንድ ትውልድ ውስጥ ያሉና በወጣቶች የተወከሉ ሦስት የተለያዩ አካላት፤ በጥሪው ዙሪያ ተሟግተዋል፡፡
የታክሲ ሹፌሮች፣ ረዳቶች፣ የጐዳና ተዳዳሪዎች መሰሎቻቸውን የወከሉት ወጣቶች፤ ሠርቶ መኖርና ተደስቶ ውሎ ለማደር ላይ ትኩረት ቢያደርጉም፤ በልዩነት የሚነታረኩ ትውልዶች ወደ ጋራ ጉዳይ እንዲመጡ፣ የተበታተኑ እንዲሰባሰቡ፣ የተሻለው እውነት እንዲያሸንፍ… ፍላጐታቸውን ከማሳየታቸውም በላይ መታገዝ ካለበት ጋር በአጋርነት ሲቆሙ ታይቷል፡፡
ሁለተኛው ቡድን በፌስ ቡክ (facebook)  ትውልድ የተወከሉት ናቸው፡፡ “ፎቶግራፍሽ ያምራል”፣ “አንተም ታምራለህ”፣ “ዓይኖችሽ ውብ ናቸው”፣ “ያንተም” የሚሉትን ለመፃፃፍ የአማርኛ ቋንቋ ፊደላት በዝተዋልና መቀነስ አለባቸው ብለው ያምናሉ፡፡ ፊደላቱ ብቻ ሳይሆኑ የሥማችንም መጠሪያ ማጠር አለበት በሚል ከሁለት ፊደል ያልበለጠ (ያውም የእንግሊዝኛ) መጠሪያ ለራሳቸው የሰጡ ናቸው፡፡ ስማቸው ትርጉም፣ መልዕክትና ክብር ኖረው አልኖረው የሚያስጨንቃቸው አይደሉም፡፡
በወጣቶች የተወከለው ሦስተኛው ቡድን፤ “አይን” የሚለው ቃል በዓይኑ “ዓ” መፃፍ አለበት ብሎ ሽንጡን ገትሮ የሚከራከር ነው፡፡ ቃላት የበዙበት ስያሜ ያለምክንያት አልተሰጠም ብለው ያምናሉ። ምክንያታቸውንም ያቀርባሉ፡፡ ያወቁትንም ሌላው ዘንድ እንዲደርስ ይጥራሉ፡፡ የብራና ሰነድና መፃሕፍት መጥፋት፣ መሰረቅና መቃጠል ዜና ሲሰሙ መርዶ እንደተነገራቸው ያዝናሉ፡፡
በአንድ ዘመን፣ በአንድ በአገርና ትውልድ ውስጥ፤ የተገኙት ወጣቶች ስለ ጥንታዊ የአገር ጥበብ ያላቸው ዕውቀትና መረዳት በሦስት የተለያዩ ገፀባህርያት (ቡድኖች) ወክሎ የሚያሳየው ሙዚቃዊ ተውኔት የሚያበቃው “አያ ቶኔ ቶር”ን የሚደግፉ ወጣቶች ቁጥር መበርከቱን በማሳየት ነው፡፡
ከዕለቱ ዝግጅት በሁለተኛነት ትኩረት ሳቢ የነበረው የሙዚቃ ግጥም ፀሐፊው ገጣሚ ሙሉጌታ ተስፋዬ የተዘከረበት ሁኔታ ነው፡፡ ለብዙ ድምፃዊያን የዘፈን ግጥሞች እንደሰጠ የተነገረለት ገጣሚው፤ “የባለቅኔ ምህላ” በሚል ርዕስ “በስንዱ አበባ አሳታሚ” ከታተመው መድበል የተመረጠ ግጥም ቀርቦለታል፡፡
ሦስተኛውና በምሽቱ ከቀረቡት ፕሮግራሞች ሁሉ ታላቅ የነበረው ደግሞ የደራሲ፣ ሐያሲና ወግ ፀሐፊው መስፍን ሀብተማርያም “የቡና ቤት ሥዕሎች” መጽሐፍ ታትሞ ለአንባቢያን መቅረቡ መበሰሩ ነው፡፡ “የብራና ልጆች” የቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጆች መጽሐፉ ዳግመኛ  ስለታተመበት ዓላማና ምክንያት ሲገልጹ፡-
“የብራና ልጆች አንደኛ ዓመት ክብረ በዓልን ስናከብር በየዓመቱ አንድ ደራሲን በተለየ ሁኔታ ማክበርና ማመስገን ስለምንችልበት ሁኔታ መክረንበት ውሳኔ ላይ ደረስን። የዘንድሮ ተመስጋኛችን ሁለገቡ የብዕር ሰው መስፍን ሀብተማርያም ሆነ፡፡ የውጭ አገር ትምህርቱን አጠናቆ በመጣ ማግስት ያገኘውን ዕውቀት ለወገኖቹ ሊያካፍል ጽፎ ያሳተመው መጽሐፍ ዓይነቱ በምን ክፍል ይመደብ? መጠሪያ ስያሜውስ ምን ይባል? በሚል ከመነሻውም የብዙ የዘርፉ ምሁራንን ትኩረት ስቧል፡፡ በወግ ምንነትና ጀማሪነት ዙሪያ ዛሬም አነጋጋሪ ሀሳቦች እየቀረቡ ነው፡፡ የዚህን ባለውለታ ደራሲ መጽሐፍ አሳትመን በመሸጥ፤ ገቢውን ለቤተሰቡ ሰጥተን ማመስገን በመፈለጋችን ነው “የቡና ቤት ሥዕሎች” መጽሐፉን ያሳተምንለት። የብዙ አካላት እገዛና ትብብር መሻታችን እውን እንዲሆን ረድቶናል” ብለዋል፡፡ በመጪው ሐምሌ 7 ከዚህ ዓለም በሞት ከተለየ አንድ ዓመት የሚሞላው ደራሲና ወግ ፀሐፊ መስፍን ሀብተማርያም፤ “የብራና ልጆች” ያሳተሙለት መጽሐፉ በተመረቀበት ሥነ ሥርዓት ላይ ደራሲ አፈወርቅ በቀለ ባደረጉት ንግግር፤ “ሁልጊዜ እንደምለው ወጣቱ ትውልድ በግጥም፣ በሥዕል፣ በድርሰት…ትንታግ ነው፡፡ በሁሉም ዘርፍ ትንታግ ሆኖም ይቀጥላል፡፡ የብራና ልጆችን ጥረትና ዓላማ ለማገዝ፣ በነፃ የተሰጠኝን “የቡና ቤት ሥዕሎች” መፅሐፍ ዋጋውን እጥፍ አድርጌ በመክፈል፣ ተባባሪያችሁ መሆኔን አረጋግጣለሁ” በማለት 50 ብር ለሚያወጣው መጽሐፍ አንድ መቶ ብር ከፍለዋል፡፡  

Published in ጥበብ
Page 13 of 16