አትሌት ሃይሌ ገብረ ስላሴ በኬንያ ሰላምን ለማስፈን ታስቦ በተዘጋጀውና በአጠቃላይ 800 ኪሎ ሜትሮችን በሚሸፍነው የሰላም ጉዞ የተሰኘ የታዋቂ አትሌቶች የእግር ጉዞ ላይ እንደሚሳተፍ ዘ ጋርዲያን ረቡዕ ዘገበ፡፡“የዜጎች መገደልና ከመኖሪያ ቤታቸው መፈናቀል በሁላችንም ልብ ውስጥ ጥልቅ ሃዘን የሚፈጥር ነገር ነው” ሲል ባለፈው ሳምንት ለጉዳዩ የሚሰጠውን ትኩረት ያሳወቀው ሃይሌ፣ በኬንያ ሰላምን ለማስፈን ታስቦ በሚከናወነው የሰላም ጉዞ የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ እንደሚሳተፍ መግለጹንም ዘገባው ገልጧል፡፡ኬንያውያን ሰላምን ጠቀሜታ እንዲገነዘቡና በተለይም በአገሪቱ ሰሜናዊ አካባቢዎች የሚታየውን የጎሳ ግጭት ለመግታት የሚያስችል አገራዊ ንቅናቄ ለመፍጠር ታስቦ የተዘጋጀው ይህ የሰላም ጉዞ፣ በመጪው ነሃሴ ስድስት ቀን የሚጠናቀቅ ሲሆን ሃይሌም በእለቱ በሚደረገው የመጨረሻው ጉዞ እንደሚሳተፍ ይጠበቃል፡፡
የማራቶን የአለም ክብረወሰን ባለቤት የሆነውን አትሌት ፖል ቴርጋት ጨምሮ ታዋቂ ኬንያውያን
አትሌቶች የሚካፈሉበት ይህ የሰላም ጉዞ፣ በሰሜናዊቷ የኬንያ ከተማ ሎድዋር ባለፈው ረቡዕ የተጀመረ ሲሆን፣ ለ24 ተከታታይ ቀናት በየቀኑ 40 ኪሎ ሜትሮችን በመሸፈን በአጠቃላይ 836 ኪሎ ሜትሮችን ይሸፍናል ተብሏል፡፡አትሌቶቹ በጉዞው ከ250 ሺህ ዶላር በላይ ገንዘብ በማሰባሰብ በአገሪቱ ተለያዩ አካባቢዎች ለሚከናወነው የሰላም ማስፈን ፕሮግራም ለመለገስ ማቀዳቸውንም ዘ ጋርዲያን አክሎ ገልጧል፡፡በህገወጥ የሰዎች ዝውውር የተጠረጠሩ 15 ኢትዮጵውያንን በኬንያ ታሰሩበኬንያ በህገ-ወጥ የሰዎች ዝውውር ተግባር ላይ ተሰማርተው ሲንቀሳቀሱ ነበር ተብለው የተጠረጠሩ 15 ኢትዮጵውያን ባለፈው ረቡዕ ኢምቡ በተባለችው የኬንያ ከተማ በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸውን ኢንቲቪ ኬንያ ዘገበ፡፡ ተጠርጣሪዎቹ በአገሪቱ መዲና ናይሮቢና በኢምቡ ከተማ አካባቢ በስውር በህገወጥ መንገድ ሰዎችን ሲያዘዋውሩ እንደነበር የጠቆመው ዘገባው፣ ፖሊስ የደረሰውን ጥቆማ መሰረት በማድረግ ባደረገባቸው ክትትል እንደዛቸው ገልጧል፡፡የከተማዋ ፖሊስ የአካባቢው ነዋሪዎች በሰጡት ጥቆማ ተጠርጣሪዎቹን በአንድ የበቆሎ እርሻ ውስጥ ተደብቀው እንዳሉ በቁጥጥር እንዳዋላቸውና ኢትዮጵውያን መሆናቸውን ከመግለጽ ውጭ፣ ስለተጠርጣሪዎቹ ማንነት መረጃ አልሰጠም፡፡

Published in ዜና

አንዳንድ ተረት አንዴ ተነግሮ የማይበቃውና ሰዎች ተገርተው እስኪበቃቸው የሚተረት ይሆናል፡፡ የሚከተለው ተረት የእዛ ዓይነት ነው፡፡
አንድ ቤት ውስጥ አባት፣ እናትና ህፃን ልጅ ይኖራሉ፡፡
አንድ ቀን ማታ ህፃኑ በምን እንደከፋው አይታወቅም ክፉኛ ያለቅሳል።
አባት - “አንተ ልጅ ምን ሆንኩ ብለህ ነው የምታለቅሰው?” ይሉታል።
ልጅ ለቅሶውን ይቀጥላል፡፡
እናት - “ዝም በል ማሙሽ፡፡ ዝም ካልክ የማረግልህን አታቅም” አሉት በማባባል ቃና፡፡
ልጅ አሁንም ማልቀሱን ይቀጥላል፡፡
አባት ተናደዱና፤
“እንግዲህ ዝም ካላልክ ለጅቡ ነው የምሰጥህ!”
ልጅ አሁንም ያለቅሳል፡፡
እናት ይጨመሩና፤
“ዋ! ይሄንን በር ከፍቼ እወረውርሃለሁ!”
ለካ ቤት ውስጥ ይሄ ሁሉ ሲሆን አያ ጅቦ ውጪ ቆሞ ያዳምጥ ኖሯል።
ከአሁን አሁን ህፃኑን ይጥሉልኛል ብሎ ይጠብቃል፡፡
ቀስ በቀስ ልጁ ፀጥ አለ፡፡ ባልና ሚስት ራታቸውን በሉ፡፡ ልጁን አስተኙና ተቃቅፈው ተኙ፡፡
ጅቡ ቢጠብቅ፣ ቢጠብቅ ምንም የሚጣልለት ልጅ አላገኘም፡፡
በመጨረሻም፤ ወደ በሩ ጠጋ ብሎ፤
“ኧረ የልጁን ነገር ምን ወሰናችሁ?” አለ፡፡
ባለቤቶቹ በራቸውን ቆላልፈው ለጥ ብለዋል፡፡ አያ ጅቦ ጠብቆ ጠብቆ ሊነጋበት ሲል ወደ ጫካው ሄደ፡፡
*   *   *
በማስፈራራት ልጅን ማስተኛት አይቻልም፡፡ ልጁ የተከፋበትን ምክንያት ማወቅ እንጂ ማባበልም ጥቅም አይኖረውም፡፡ በአንፃሩ እንደ አያ ጅቦ የቀቢፀ ተስፋ ምኞት መመኘትም ራስን የባሰ ረሀብ ውስጥ መክተት ነው!
በሀገራችን የተመኘናቸው የነፃነት፣ የዲሞክራሲና የፍትህ ጥያቄዎች በዱላም በካሮትም (Carrot and stick እንዲሉ) እየተሞከሩ ረዥም ዕድሜ አሳልፈዋል፡፡ ዛሬም የጠራ ጐዳና ላይ አልወጡም፡፡ የተኙ ተኝተዋል፡፡ የሚያለቅሱ ያለቅሳሉ፡፡ እንደ አያ ጅቦ ደጅ የቀሩም ይቀራሉ።
“…አሁን የት ይገኛል፣ ቢፈልጉ ዞሮ
መስማት ከማይፈልግ፣ የባሰ ደንቆሮ”
የሚለውን የከበደ ሚካኤልን ግጥም ልብ ማለት ለሀገራችን በጣም ጠቃሚ ነው፡፡
አሁንም የህዝብን ብሶት እናዳምጥ፡፡ ዛሬም ያልተመለሱ ጥያቄዎችን ለመመለስ ቀና ልቦና ይስጠን፡፡ ሌላው ቀርቶ የዓለም መንግሥታት የሚያደርጉልንን ድጋፍ ለመቀበልም ቀና ልቡና ያስፈልጋል፡፡ መረጃዎችን፣ አገራችንን የሚመለከቱ ጉዳዮችን እናውቅ ዘንድ ቀና ልቡና አለንና በወጉ የማወቅ መብታችን ሊጠበቅ ይገባል፡፡
የደረስንበት እንዳይርቅ፣ ከእጃችን ያለው እንዳይፈለቀቅ ልዩ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርብናል፡፡ ዛሬም መደማመጥ፣ መቻቻልና ዛሬም ረብ ያለው የፖለቲካ አቅጣጫና ተጨባጭ የሀገር ጉዳይን ማንሳት ይጠበቅብናል። የአሸነፈም፣ የተሸነፈም ሀገር ለምንላት የጋራ ቤት ምን ዓይነት አስተዋጽኦ እያደረግሁ ነው ብሎ መጠየቅ አለብን፡፡
ማንም ቢሆን ማን ምርቱ ይታወቃል፡፡ መንገዱም ይለያል፡፡ መሸሸግ የማይቻሉ በርካታ ነገሮች መኖራቸውን ህዝብ ያውቃል፡፡ ምክንያቱም ፍሬ ከዛፉ ርቆ አይወድም።

Published in ርዕሰ አንቀፅ

በዓለማየሁ ማሞ የተፃፈው “የህይወቴ ፈርጦች” የተሰኘ ግለታሪክ ከትላንት በስቲያ በኢትዮጵያ ቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን አዳራሽ ተመርቆ ለንባብ በቃ፡፡
ደራሲው በመግቢያው ላይ መጽሐፉን የፃፈበትን ምክንያት ሲያስረዳ፤ “ልጅነቴን፤ የትምህርት ቤት ውሎዬን ኋላም መርከበኛ፤ የጤና ባለሙያ፤ ጋዜጠኛና ደራሲ ሳለሁ ወይም እያለሁ የሆኑትን ግን አንኳር የመሰሉኝን ነው የመረጥኳቸው፡፡ ካሰብኩት ቆየሁ። በዚህም ላይ በጨዋታ መሃል የተነሱ ፈርጦችን ወዳጆቼ ስለወደዷቸው በወረቀት ላይ እንዳኖራቸው ገፋፍተውኛል፡፡” ብሏል፡፡
መጽሐፉ በዘጠኝ ምዕራፎች ተከፋፍሎ በ268 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን ለአገር ውስጥ በ80ብር፣ ለውጭ በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ፀሐፊው አለማየሁ ማሞ ነዋሪነቱ  በአሜሪካ ሜሪላንድ ሲሆን ባለፉት 17 ዓመታት ለጠቅላላ ዕውቀት የሚጠቅሙና ይልቁንም ለነፍስ ዕውቀት የሚበጁ በርካታ መፃህፍትን እንዳዘጋጀ ታውቋል፡፡

በድቅድቁ የቀለመውን ፅልመት ሃዘን በከረቸመው ከንፈሮችዋ መሃል በማትጐለጐል ነበልባል የነገን ጭላንጭል ተስፋ እያየች ትዕግስት የሚሉት ተሰጥኦ እንደዛር ተከምሮባት ከባዱን ችላ ስለምትወዳቸው መስዋዕትነት የከፈለች በእውነት ጐበዝ ጀግና ነች…”
ከላይ የቀረበው ቅንጭብ የተወሰደው ደራሲ ዝናሽ ኤልያስ (ዲና) ከጻፈችውና “መስዋዕት” የሚል ርዕስ ከሰጠችው ረዥም ልብወለድ ሲሆን መጽሐፉ ሰሞኑን ለገበያ ቀርቧል፡፡ የታሪኩ ጭብጥ በአንዲት ሴት የህይወት ውጣ ውረድ ዙሪያ የሚያጠነጥን ነው ተብሏል፡፡
“መስዋዕት” በእውነተኛ ታሪክ ላይ ተመስርቶ የተፃፈና በ214 ገፆች የተሰናዳ ሲሆን በ60 ብር ለሽያጭ እንደቀረበ ታውቋል፡፡

Saturday, 11 July 2015 13:01

ጊዮርጊስ ታዛ ስር

 ሰንበትን በዚያ ባለፈ ባገደመ ቁጥር ያያቸዋል -ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ቅጽር ስር፤ መናኛ ልብስ ለብሰው ባነጠፋት ጨርቅ ላይ ሲመፀወቱ፡፡
…ፈፅሞ ያላሰበው ቦታ ላይ ነው ያያቸው፤ ኮከብ ቆጣሪም ሊገምተው የማይችል የመሰለው ቦታ ላይ፡፡ ለማመን ተቸግሮ ነበር፡፡ ግንባራቸው ላይ የተጋደመው ጠባሳ ነው ጥርጣሬውን የከላት። እንደ መንገድ ላይ የትራፊክ መስመሮች ዘና ብሎ የተጋደመው ጠቋራ ጠባሳ!...
ሰውዬውን የማወቅ ፍላጐቱ ጣራ ነካ፡፡ አዲስ ነገር በማወቅ የሚያገኘው ደስታ ከወይን ጠጅ በላቀ ነፍሱን ያስተፈሲህለታል፡፡ ከሴት ገላ በላይ ውስጡን ያሞቀዋል፡፡
በአዲስ አበባ “የልመና ሙያ” ላይ ሊያደርግ ላሰበው ጥናት ጥሩ መነሻ እንደሚሆኑት አመነ፡፡
ከቀናት በኋላም ዘባተሎ ለብሶ፣ ፀጉሩን ከማበጠሪያ አኳርፎ ለተበጣጠሰ ሸራ እግሩን ድሮ…ወደ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን አቀና፡፡
…ከሰውዬው አጠገብ ተቀመጠ፡፡
“አዲስ ትመስላለህ…ጃል?!”
“አዎ…አባት!”
“ፊትህ የመከራ በትር ያረፈበት አይመስልም፡፡ ምን ገጠመህ ታዲያ ልጄ?!”
ያጠናውን ቃለ ተውኔት መጫወት ነበረበት፡፡
“ቤተሰቦቼ አልቀዋል፡፡ የምኖርባትን ቤት አባቴ የባንክ ዕዳ ነበረበትና መንግስት ወረሰው፡፡ እንዳልሸከም የጀርባ ህመም አለብኝ፡፡ ምርጫ ሳጣ ልለምን በቃሁ አባቴ፡፡”
ፊቱ የሀዘን ጥላ አጠላ፡፡
…በሀዘኔታ ተመልክተውት ፊታቸውን ወደ መንገደኛው መለሱ፡፡
ወጭ ወራጅ…ሂያጅ መንገዱን ሞልቶታል…ጥጋቱን  የኔ ቢጤዎች ተደርድረዋል፡፡
ቅዳሴ ይሰማል፡፡ መንገደኞች ደፋ ቀና እያሉ ያልፋሉ፤ እየተሳለሙ፡፡ ምዕመናን ነጠላ እንደተከናነቡ በሩን ይስማሉ፡፡
ገሚሶቹ ወደ ውስጥ ዘልቀው ታድመዋል፡፡
…ናሆም አዛውንቱን አስተዋለ፡፡ የተጐሳቆለ ሰውነት የላቸውም፡፡ ጠይም ፊታቸው በችግር እሳት የተጠበሰ አይደለም፡፡
“አባት…”
“አቤት ልጄ”
“እንዴት ነው ስራው?”
“ይመስገን ለፈጣሪ…ሰው ደግ ነው ይመፀውታል። የኛ ሰው ሃይማኖተኛ ነው፡፡ ፈሪሀ እግዚአብሔር ልቡ አድሯል፡፡ የተቸገረን መርዳት ልማዱ ነው፡፡ ይመስገን ለፈጣሪ ልጄ ይመስገን!”
ናሆም ስሜታቸውን ከገጽታቸው ለማጥናት እየሞከረ ያዳምጣል፡፡
እኝህ ሰው ዛሬ ያሉበት ቦታና ከቀናት በፊት የታዩበት ቦታ እጅግ የተራራቁ ናቸው፡፡ ርቀታቸው በሰማይና በምድር ሊመሰል ይችላል፡፡
ሆቴል…ጊዮን ሆቴል ሙሉ ልብስ ለብሰው…ከረባት አስረው…ከሁለት ወጣቶች ጋር ደብሊው ቢኤም የቤት መኪና እያሽከረከሩ ሲወጡ ነበር ያያቸው፡፡
ዓይኖቹ የድሮ ዓይኖቹ ነበሩ…ሰውየውም ራሳቸው፡፡
“ይቅርታ ያድርጉልኝና አባት…”
“ምነው ልጄ?!”
“ምን ያህል ጊዜ ሆነዎ?”
“ምኑ?”
“እዚህ ቦታ መቀመጥ ከጀመሩ…”
የውሃ ጠብታ ድንጋይ እንዲሰብር… ቀስ በቀስ ነው…. የምስጢሩን ቅርፊት መስበር የፈለገው፡፡ ለዘብተኛ ሆኖ በልዝብ ቃላት ወደ ግቡ እያዘገመ ነው፡፡  
“ይመስገን ፈጣሪ…ይኸው ሶስተኛ ዓመቴ መጣ።” ፊታቸውን አነበበ፡፡ ኩራትና ትካዜ የተዳቀሉበት መጢቃ ስሜት!
“ቤተሰብ …ልጆች የለዎትም?”
“ኧረ አለኝ ልጄ…ምን የመስሰሉ ሁለት ሸበላዎች አሉኝ…”
ቃላት እየመረጠ…ጥያቄዎችን ከመልሶቻቸው ስር ስር ማሶክሶክ ቀጠለ፡፡
“…አሀ …ታዲያ ከዚህ ከምፅዋት የሚገኝ ገንዘብ ከነቤተሰብ ያኖራል?!”
“እሱስ አዎ! የኛ ሰው ቸር ነው ብዬህ የለ!?”
“እህ …ታዲያ ልጆችዎ ምንም አይሰሩም?”
መልስ ለመስጠት ዘገዩ፡፡
“አባቴ!”
“አቤት ልጄ”
“ሰምተውኛል?”
“እ?”
“ልጆችዎ አይሰሩም?”
“…ይሰራሉ’ንጂ…ይመስገነው ለፈጣሪ የሁለት ድርጅቶች ስራ አስኪያጆች ናቸው፡፡”
“ምን አሉኝ?”
ሰምቷል፡፡ በደመነፍስ ነው መጠየቁ፡፡
“ሁለቱም ልጆቼ ጥሩ ስራ አላቸው፡፡ ስራ አስኪያጆች ናቸው…ክብሩ ይስፋ ለመድኃኒዓለም!”
“ምን ድርጅት ውስጥ ነው የሚሰሩት?”
“የግል ድርጅት ነው ልጄ”
“የማን ናቸው ድርጅቶቹ?”
“የኔ!”
የናሆም ግርምት እንደ ርችት ወደ ሰማይ ተተኮሰ።
“የ‘ርስዎ?!”
“አዎ ልጄ”
መደመሙን መደበቅ አልቻለም፡፡ ድብን ካለ ገጠር ወጥቶ መኸል ከተማ እንደተጣለ ባላገር ድንብርብር አለው፡፡ የአምልኮ ስርዓቶችን በቅጡ ሳይረዳ ቤተ አምልኮ እንደገባ አዲስ አማኝ ብዥ አለበት፡፡
“እና…እንዴት …ለምን?”
መጨረስ ከበደው፡፡
“እንዴትና ለምን ትለምናለህ ልትለኝ ነው?”
“ገብቶዎታል አባቴ”
“ሰፊ ታሪክ አለው፡፡” አሉ ጌሾ ወቅጠው እንደጋቱት ሰው ፊታቸውን አኮምጭጨው፡፡
“እባክዎን ባጭሩ ያጫውቱኝ?!”
አትኩረው ተመለከቱት፡፡ ከፍተኛ የማወቅ ጉጉት!
የተደበቀ ነገር በመግለጥ የሚረካ የሚመስል ትጉህ ወጣት!
“ይኸውልህ ልጄ…ልጆቼን እንደ አባትም እንደ እናትም ሆኜ ያሳደግኋቸው እኔ ነኝ፡፡ እናታቸው ገና ነፍስ በማወቂያቸው ዋዜማ ነው የሞተችብኝ!...”
በትካዜ ተዋጡ፡፡ በትዝታ መርከብ ተሰፈሩ፡፡ ከሰኮንዶች በኋላ፤
“…እንግዲህ በህይወቴ ያሉኝ እነዚህ ልጆች ብቻ ናቸው፡፡ ዘመድ አዝማድ ያለኝ! ሚስት የለኝ! ቢሆንም በልጆቼ ደስተኛ ነበርኩ፡፡ ታዲያልህ በአንድ የተረገመ ቀን ናዝሬት ቅርንጫፍ ላለው የንግድ ድርጅቴ ከመጀመሪያው ልጄ ጋር ዕቃ ጭነን ስንጓዝ የጭነት መኪናው ፍንግል አለ…”
አሁንም በዝምታ ቡልኮ ተጆቦኑ፡፡ “ሩቅ እንደሚያስቡ ያስታውቃሉ!” አለ ናሆም፡፡
“እኔ ይች ጭረት ነበረች ጉዳቴ” ግንባራቸው ላይ የተጋደመውን ጠባሳ እየጠቆሙት፡፡
“ለክፉ አልሰጠኝም፤ ልጄ ግን ክፉኛ ተጐዳ፡፡
ለሳምንት ነፍሱን አያውቅም ነበር፡፡”
መተከዙን አላቆሙም፡፡ አንድ ዐረፍተነገር ሲያገባድዱ አራት ነጥባቸው ቁዘማ ነው፡፡
“ሳሳሁ!...ሳሳሁ ልጄ ጨነቀኝ፡፡ ይሕን ልጄን ማጣት የዓይኔን ብርሃን ማጣት ሆነብኝ…ልቤን ማጣት ሆነብኝ…እናም…ለቅዱስ ጊዮርጊስ ተሳልኩ፡፡”
“ምን ብለው?”
“ልጄን በህይወት ካተረፍክልኝ ለአምስት ዓመት ያህል በሳምንት ሰንበት ለምኜ ገንዘቡንም ለቤተክርስቲያንዋ ገቢ እንደማደርግ ተሳልኩ!
ወደ ላይ አንጋጠው፤
“ሞገስ ይብዛ ለአምላክ…ልጄ ከነሙሉ ጤንነቱ ተነሳልኝ”
ናሆም በነገሩ እየተደመመ፤ “ደህና ይሁኑ” በማለት ቦታውን ለቀቀ፡፡ ፈጽሞ ያልጠበቀው ነገር ቢገጥመውም ቤቱ የደረሰው “ለጥናቴ ጥሩ መንደርደሪያ አገኘሁ” ብሎ እያሰበ ነበር፡፡

Published in ልብ-ወለድ

     ፊት ለፊት ስራው፣ ከበስተጀርባ ደግሞ ህይወቱ ይገኛል፡፡ ሥራው የህይወቱ ማጣቀሻ ነው የሚሉ አሉ፡፡ በዚህም ሥራውን እንደ አነፍናፊ ውሻ አስቀድመው ህይወቱን ያንጎዳጉዳሉ፡፡ “እንዲህ ሲል የፃፈው በህይወቱ እንዲያ ስለሆነ ነው፡፡” በማለት ሥራና ህይወቱን ያጋባሉ፣ ያፋታሉ፡፡ ስለዚህ የደራሲ ቤት በሩ ቢዘጋም ከመግባትና ከመውጣት አይከላከልም፡፡ የደራሲ ደጃፍ ውሻ ቢታሰርበትም አያስፈራም፡፡ ቢታጠርም ከዘላዮች አያመልጥም፡፡
እኛ ዘንድ እንዲያ ለማድረግና ለመሆን የሚያስችል ሁኔታ የለም፡፡ ደራሲ የጓዳ ህይወቱ ቀርቶ አደባባይ የዋለው ሥራው እንኳን “በሙሉ አይን” አይታይም። ሀዲስ አለማየሁ፣ በዓሉ ግርማ፣ መንግሥቱ ለማ፣ ከበደ ሚካኤል፣ ፀጋዬ ገብረመድህን… የኖሩት ቀርቶ የፃፉትም የሚታየው በእሽኩርምሚት ነው። ከሥራዎቹ ፊት “ተልመጥማጮች” ያጠሩት የሙዚየም “ክር” አለ፤ አይታለፍም፡፡ የፅሁፍ ማስጠንቀቂያም አለ፤ “በእጅ መንካት ክልክል ነው” የሚል፡፡ እኔ የሚገርመኝ “የተልመጥማጮቹ” በክር ማጠርና መንገር አይደለም፡፡ የእኛ አክብሮ ሥነ - ፅሁፍን በሙዚየም ህግ መጎብኘት እንጂ …፡፡
“የሀዲስ ዓለማየሁ ፍቅር እስከ መቃብር ተረታማ ነው” ከተባለ “ቱግ” የሚሉ “አንቀራባጮች” አሉ። “በዓሉ ግርማ ልቦለድ ያድፋፋል፤ አጨራረሱ መሰላቸት የሚታይበት የተካለበ ነው” ከተባለ የሥራው “ተሸላሚዎች” ፣ “ሐይማኖት የግል ነው፣ ለምን ይነካብናል?” በማለት ህገ መንግሥት መጥቀስ ይዳዳቸዋል፡፡ “የመንግሥቱ ለማ ግጥሞች ጥብቀትና ፍላት የሌላቸው በተሃ ናቸው” ከተባለስ? ጉዳዩን የቤተሰብ ፖለቲካ አድርገው “አብዬን?” የሚሉና የዛገ ጦር ከራስጌ የሚመዙ ሞልተዋል፡፡ “ከበደ ሚካኤል መከሩ፣ ዘከሩ እንጂ አልተቀኙም” የሚል ካለ፣ “ባባቶቻችን ደም” ይዘፈንበታል፡፡ “ፀጋዬ ገብረመድህን ግጥም እንጂ ዝሩው ያዳግተዋል” ብሎ በህይወት መኖር ያዳግታል …
የእኛ ሥነ - ፅሁፍ መብላላት ሲገባው የሚደነብሸው ለዚህ ሳይሆን ይቀራል? ገንዘብ ያወጣሁበትን መፅሐፍ ለመግዛት፣ ጊዜ ያፈሰስኩበትን ልቦለድ (ለማንበብ)፤ ቦታ የሰጠሁትን ሥራ ለማስቀመጥ … እንዴት በሌሎች እይታ እንድገመግመው እገደዳለሁ? እንዳቅሜ ከቻልኩ “ብበላው”፣ ካልቻልኩ “ብደፋው” ከውይይት ያለፈ ከሳሽና ወቃሽ ሊመደብብኝ ይገባል?...
… እንደውም ከሥራዎቹ አልፈን ደራሲዎቹ ህይወትና ኑሮ ላይ ብንሳፈር “ውረድ!” ባይ እልፍኝ አስከልካይ ሊመደብብን ይገባል? ስለ ሀዲስ ዓለማየሁ ብህትውና፣ ስለ በዓሉ ግርማ ውሎና አዳር፣ ስለመንግስቱ ለማ ሽሙጥ፣ ስለ ከበደ ሚካኤል የኩርፊያ ኑሮ፣ ስለ ፀጋዬ ገብረመድህን የተመላኪነት መንፈስ … ማውራት ግለሰብ ማውሳት ነው?...
ዮሐንስ አድማሱ ስለ ደራሲ ማውሳት ግለሰብ ማማት ተደርጎ እንዳይወሰድ የሚዘክር ተቀዳሚ ገጣሚ ነው፡፡ ስለ ዮፍታሔ ንጉሴ በቀረበው ጥናት ላይ የባለቅኔውን “የቆንጆ ፀርነት” ከማውሳት አልፎ እናቱ “ሒያጅ” እንደነበሩ ይጠቅስና እንዲህ ይላል፤
“ዮፍታሄን እንዲህ ማንሳቴ አለመልኩ እንዳይመለክ፣ አለግብሩ እንዳይወቀስ፣ እንደ ግዑዝ እንዲታይ ነው፡፡”
ዮሐንስ “እንደ ግዑዝ” ሲል ምን ማለቱ ነው? እንደ ዕቃ? እንደ ሀውልት? ወይስ ምን? ብለን እንጠይቅ። ዮሐንስ ማለት የፈለገው ዮፍታሄ እንደ ግለሰባዊ ህልው፣ አድራሻና መዳረሻ እንዳለው ሳይሆን ለመወያያ ወደ ሀሳብነት ደረጃ ከፍ አድርገን፣ የሰው ልጅ ምስጢር ማስተንተኛ ይሁነን ነው፡፡ ደራሲን “ከሰውነት” አውጥቶ ወደ “ሀሳብነት” ማሳደግ፣ ለህብረተሰብ አውጠንጣኝነት የሚበጅ ነው፡፡ እኛ ግን ለዚህ አልታደልንም፡፡
በተለይ ጥቂቶቹ ደራሲዎቻችን ከዚህ ዓለም በሞት ከተለዩ በኋላ በሥማቸው የሥነ ፅሁፍ ደብር ይደበርና ጭፍን አምልኮ ይካሄድባቸዋል። አለመልኩ ይመለካሉ፤ አለግብሩ ይዘከራሉ፤ አይመረመሬ ይሆናሉ፡፡
ይሄን አምልኮ ለመሻር በማሰብ ይመስላል ብርሃኑ ዘሪሁን “አዲስ ዘመን” ጋዜጣ ላይ ስለ ደራሲዎች ቁርቁስ ተከታታይ መጣጥፍ አቅርቦ ነበር፡፡ በተለይ መንግሥቱ ለማ እና ፀጋዬ ገብረመድህን ያላቸውን የፉክክር “አተካራ” አጠንክሮ ጠቅሶታል፡፡ ስለዚህ ጉዳይ የተጠየቀው ጸጋዬ ገብረመድህን፤ “ጦቢያ” መፅሄት ላይ እንዲህ በማለት መልስ ሰጥቶ ነበር፡-
“… ወዳጄ ብርሃኑ ዘሪሁን ነበር በተለመደ ቅንነቱ በሥነ - ፅሁፍ ዓለም የደራሲያን መከራከርና መወዳደር ሙያውን ያዳብራል፣ የአንባቢውንም ህዝብ ጣዕምና ግንዛቤ ያካብታል በሚል ትክክለኛ ሀሳብ ተነስቶ፣ በአዲስ ዘመን አምድ ላይ “የደራሲያን ጦርነት” ብሎ ያስቀመጠው መልዕክት፣ እሱም እኛም ወደ አላሰብነው አቅጣጫ ሄዶ፣ ለከተሜው የቧልት ፍጆታ ሆነ፡፡ እስከዛሬ “ጦርነት” እየተባለ “በምሁራን” አካባቢ ይቧለትበታል፡፡ እንጂ ከወዳጄ ከመንግስቱ ለማ ጋር እንኳን ጦርነት ቁርቋዞም አልነበረንም”
ፀጋዬ ይሄን ይበል እንጂ መለስ አድርጎ ስለ መንግስቱ ለማ ቀልድ ለበስ ንግግር ሲገልፅ አንዳች ነገር እንደነበር ለመጠርጠር እንገደዳለን፡፡
“… እኔ ከገጠር ሜጫ ምድር ከገበሬና ከመለስተኛ ነጋዴ ቤተሰብ መጥቼ፣ አዲስ አበባ በምኒልክ ከተማ፣ ብዙ የሥነ ፅሁፍ ታላላቅ ሰዎች በታወቁበት፣ በደረጁበትና ሥር በሰደዱ መሀል ገብቼ፣ ገና በሀያ ዘጠኝ ዓመቴ ስሸለም፣ የነፍሳቸውን መክሊት እንደወሰድኩባቸው ያህል በተለይ ጉምቱዎቹ የሥነ ፅሁፍ አባቶች ያደረሱብኝን የምቀኝነት ቁስል በቁጭት ሳስታውሰው፣ የወዳጄ የመንግሥቱ ለማ ደማም ቅሬታ፣ እንኳንስ ሊያማርረኝ እንደቅድመ ማስጠንቀቂያ ምክር ነበር የጠቀመኝ፡፡ በዛሬው ጊዜ ታዲያን እንደመንግስቱ ለማ ደማም ቀልደኛ፣ ኮሶውን ከማር ለውሶ ማሻር የሚያውቅበት ደራሲ ስለጠፋ ነው፣ የጭቃ ጅራፍ ለጣፊና የጭቃ ጅራፍ “ተለጣፊ” ብቻ የተንሰራፋው፡፡ ያም ሆኖ የመንግስቱም ቀልድ አንዳንድ ጊዜ መራራ ነበር፡፡”
ሥነ ፅሁፋዊው “በደረቁ እጥበት” የደራሲዎቻችንን ህይወት አንፅቶ የአደባባይ ክት - ልብስ አደረገው እንጂ በየስርጉጡ የተነካካከ ነበር። የሚገርመው በላውንደሪ ሥራ መጠመዳችንና በማንፃት ሥራ መለከፋችን የነበረው እንደነበረው የማቅረብን ያህል የሚጠቅመን አልነበረም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ብቅ የሚሉ መረጃዎቻችንን ስንመረምር፣ ፀጋዬ ቁርቁሱን እጅግ አድርጎ እንዳለዘበው ይገባናል። የሥዕልና የሥነ-ፅሁፍ ሀያሲው ስዩም ወልዴ “ኩርፊያ የሸፈነው ፈገግታ” የተሰኘ መፅሀፉ ውስጥ ስለዚሁ የደራሲያን የመሸራደድና የመጠቃቃት ባህርይ ይነግረናል፡፡ ከበደ ሚካኤል የአፄ ኃይለሥላሴ ሽልማት ድርጅት ሲሸልማቸው፣ ደራሲ ዓለማየሁ ሞገስ በዚሁ በሽልማቱ ጉዳይ ስብሰባ ጠሩ፡፡ ወወክማ ለታደመው ሰውም በአደባባይ “ከበደ ደራሲም ተርጓሚም አይደለም፡፡ ከበደ ሌባና ባንዳ ነው” እንዳሉ ስዩም ወልዴ ነግሮናል፡፡
እንኳን የጓዳው ህይወት እንዲህ ያሉ የአደባባይ መግለጫዎችም ያለተፈጥሯቸው ውስጥ ለውስጥ እንዲስለከለኩ እያስገደድናቸው ነው። ለምን? ለማን? … ደራሲዎቻችንን ከህልፈት በኋላም፣ ሲወጓቸው እንደሚደሙ፣ ሲነግሯቸው እንደሚደመሙ ከማሰብ፤ እንደ ዮሐንስ አድማሱ ወደ ሀሳብ ደረጃ አሳድጎ፣ አጠቃላይ የሰው ልጅን ማጥኛ ማድረግ አይበጅም? እኔ ይበጃል ባይ ነኝ፡፡

Published in ጥበብ

የዘንድሮ የትምህርት ጊዜ ማብቃትን ምክንያት በማድረግ “ኑ እናንብብ” የተሰኘ የተማሪዎች የክረምት የመፅሃፍ ንባብ፣ የባህልና የኪነ ጥበብ ፌስቲቫል ሐምሌ 11 እና 12 በአዲስ አበባ የስብሰባ ማዕከል እንደሚካሄድ ተገለፀ፡፡
በፌስቲቫሉ ላይ ከ30 በላይ በመፅሀፍ ህትመትና ሥርጭት ላይ የተሰማሩ ድርጅቶችና ከ20 በላይ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች ተሳታፊ ይሆናሉ ተብሏል፡፡ በሁለት ቀን ፌስቲቫሉ ላይ አንጋፋና ወጣት ደራስያን፣ አርቲስቶችና ምሁራን ለህፃናትና ወጣቶች መፃህፍት የሚያነቡ ሲሆን የህፃናት ቴአትሮች፣ መዝሙሮች፣ ፊልሞች፣ የፖፔት ትዕይንቶች እንዲሁም የባህልና ታሪክ የማስተዋወቂያ ዝግጅቶች እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም የሥነ - ፅሁፍ፣ የስዕልና የተሰጥኦ ውድድሮችም ተዘጋጅተዋል፡፡
የፌስቲቫሉ ዋና ዓላማ ተማሪዎች የንባብ ባህላቸውን እንዲያዳብሩ ግንዛቤ መፍጠር ሲሆን ከተለያዩ የሙያ መስኮች የተጋበዙ ስኬታማ እንግዶችም የህይወት ልምዳቸውንና የንባብ ጠቀሜታን በተመለከተ ተመክሮአቸውን ለተማሪዎች እንዲያጋሩ ማድረግ ነው ተብሏል፡፡
የተማሪዎች የክረምት ፌስቲቫሉን በኢቢኤስ ቴሌቪዥን “የኢትዮጲስ ጊዜ” የተሰኘ የህፃናት ፕሮግራም አዘጋጅ የሆነው አማራጭ ሚዲያና ኢንተርቴይመንት ከአዲስ ምዕራፍ ፕሮሞሽን ጋር በመተባበር እንዳዘጋጁት ለማወቅ ተችሏል፡፡

ጽልመት በለበሰ እልፍ አዕላፍ የሰው ዘር ላይ እንደ መርግ ለመጫን የሚንደረደር ብይን መስጫ መዶሻ ከመጽሓፉ ልባስ ላይ ታትሟል፡፡ የልባሱ ገጽታን ተመልከተን የሚፈጠርብን ብዥታ የለም። አንዴ ገርመም አድርገን የፍሬ ነገሩ መቋጫን ለመተንበይ ብዙ መራቀቅ አይጠበቅንብም፡፡
መንደርደሪዬ የአለማየሁ ገበየሁ የረከሰ ፍርድ በኢትዮጵያ መጽሐፍን ይመለከታል፡፡ መጽሐፉ በ189 ገጾች  የተቀነበበ ሲሆን በውስጡ ካቀፋቸው አስራ አራት አጫጭር ታሪኮች ፣ መጣጥፎች እና ዘገባዎች የፊትአውራሪነትን ካባ የለበሰው አንሳርማ የተባለው የፋንታሲ አጻጻፍ ስልትን የተከተለ ምናባዊ  ፈጠራ ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ የአጻጻፍ ዘይቤ የጆርጅ ኦርዌልን Animal farmን ያስታውስናል፡፡
አንሳርማ ገና ከጅምሩ ጠንከር ባለ መፈክር ነው የሚቀበለን፡፡
‘ከአሳማዎች አስተዋይ አመራር ጋር ወደ ፊት’
ከእልፍኙ እንደዘለቅን በገጽ 24 ላይ ራዞር የተባለው አሳማ አስገራሚ ዲስኩሩን ይጋብዘናል፡-
“ጓዶች! እንደምታውቁት ሕገ መንግሥታችን የተዋቀረው ሁሉም እንስሳት እኩል ናቸው በተባለው ፍልስፍና ላይ ነው፡፡ ይህ መርህ መቼም ቢሆነ አይሸራረፍም፡፡ ኾኖም ይህን ድፍን ሐሳብ እንደ አትላስ ተሸክሞ ሥራ ማከናወን አይቻልም። ለዚህም ነው ለረጅም ጊዜ ስንሠራ የቆየነው፡፡ የከተማችን ስያሜ፣ባንዲራችንና ብሔራዊ መዝሙራችን እስካሁን የሠራናቸው የማስፈጸሚያ ስልቶቻችን አካላት አድርጎ መውሰድ ይቻላል፡፡ በዋናነት ደግሞ የአፈጻጸሙ መመሪያ “ሁሉም እንሰሳት በመርህ ደረጃ እኩል ናቸው፤ነገር ግን አንዳንድ እንስሳት ከሌሎች ከእኩል በላይ ሊሆኑ ይችላሉ” ተብሎ መደንገጉን ሳበስር በደስታ ነው፡፡”
አንሳርማ እና የጆርጅ ኦርዌል “አኒማል ፋርም” የሚያስተላለፉት ጭብጥ፣ የሚንደረደሩበት መላምት እና የሚደርስቡት ድምዳሜ ኩታገጠም ነው፡፡ አንሳርማም ሆነ አኒማል ፋርም ዙሪያ ጥምጥም አይሄዱም፡፡ በአሳማ ዝርያ የተመሰለን አጓጉል ሰብዕናን በጥበብ ሾተል እየዋጋጉ የተደራሲያንን ንቃት ከከፍታ ላይ ለመስቀል ተፍ ተፍ ይላሉ፡፡ ከአሳማ ዘር ጋር በአንድ ማሕጠን የተኙት ራስ ወዳድ እንደራሴዎች በእዚህ ዓይነቱ የጥበብ አውድ ላይ ሲበለቱ ማየት ለአንባቢው የሚፈጥረው ስሜት የላቀ ነው፡፡
ደራሲው በአንሳርማ ምህዋር ላይ እንድንሽከረከር ምናባዊ መንኮራኮር ፈብርኮልን ነበር፡፡ ግና አመስግነነው ከአፋችን ሳንጨረስ ምናባዊው ጉዞው እክል ገጥሞት ቁልቁል ያምዘገዝገናል። የተከናነብነው የጥበብ ጃኖ ከላያችን ላይ ተገፎ በቅጽበት በቆፈን እንኮማተራለን፡፡
ተዓምረኛው የቅንጅት ምልክት  በሚለው ታሪክ ሥር አቧራ የጠገቡ ችኮ ዘገባዎች የአንሳርማን ሙቀት ተሻምተው ከፊት ለፊታችን ገጭ ይላሉ፡፡ ፀሐፊው የታሪኩ አሰላለፍ ብዙም ግድ የሰጠው አይመስልም። በአንሳርማ እግር የተተካው ታሪክ ፍዝነቱ የበዛ ነው። ጭልጥ ካለ ምናባዊ ፈጠራ ወደ አረጀ አፈጀ ደረቅ ዘገባ በመንደርደራችን የተነሳ በጋመው ስሜታችን ላይ ቀዝቃዛ ውኃ ይቸለሳል፡፡ የመጽሐፉ ገዢ ርዕስ የአንሳርማን እግር ተከታይ ቢሆን ኖሮ ሚዛናዊ ስሜት በመፍጠሩ ረገድ የሚታማ አይሆንም ነበር። አንሳርማ እና የረከሰ ፍርድ ሰም እና ወርቅ ናቸው። አንሳርማ “ስክሪፕት”፣ የረከሰ ፍርድ ተውኔት ነው፡፡ እነዚህ ተደጋጋፊ ታሪኮች እግር በእግር እንዳይከታተሉ የይለፍ ፍቃድ ተነፍገዋል፡፡
ደግነቱ ደራሲውን ብዙም ሳናማው መልሶ ይክሰናል፡፡ በጥበብ ማጀቱ ከቋጠረው ጥሪት ያለ ስስት እያቃመሰን የዳመነውን  ገጽታችንን ለማፍካት ይተጋል፡፡ የግብዣ ማግደርደሪያውን በገጽ 52 ላይ እናገኛለን፡-
“ማስታወሻ ደብተሬን በገለበጥኩ ቁጥር ፊቴ ፈገግ፣ቅጭም ይል ነበር፡፡ ገጹን እንዲህ የሚቀያይረው አስደሳች፣አስገራሚና አሳዛኝ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በጉዳዮቹ ውስጥ ደግሞ መረጃ የሚሰጡ ሰዎችና የሚጠይቁ ጋዜጠኞች አሉ፡፡ በዜና ካበጡ በርካታ መረጃዎች ውስጥ የንባብ ብርሃን ያላገኙትን ጥቂቶቹን መራርጬ እነሆ እንድታነቧቸው ጋበዝኳችሁ፡፡”
በአለፍ ገደም የተቃረሙት እውነታዎች በእርግጥም የባለሙያ እጅ የጎበኛቸው ክሽኖች ናቸው፡፡ አንዳንዴም ፊታችንን ቅጭም እያደረገን አንዳንዴም በፈገግታ እየተደነቃቀፍን ከገበታው እንቋደሳለን፡፡ ገጽ 54 ላይ ይህ ግርምት ተከትቧል፡-
“ቦታው አዲስ አበባ ነው፡፡ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት /መኢአድ/ አጠቃላይ ስብሰባ ጠርቶ በተለያዩ ርዕስ ጉዳዮች ላይ አባላቱ ውይይት እያደረጉ ነው፡፡ አንዳንዴ ከዋና ርዕስ ያፈነገጡ አንዳንድ ጉዳዮች ሳይታሰብ ቦግ ብለው ይወጣሉ፡፡ አንዳንድ አባላት አስተያየት ከሚሰጡበት ዋና ጉዳይ አስቀድመው እንደ አፍ ማሟሻ ይሁን ነገር ማጣፈጫ በስሜት የሚናገሯቸው ቃላት ትኩረት ሳቢና ፈገግታ ጫሪ ናቸው፡፡
አንድ ታሳታፊ እድሉ ከተሰጣቸው በኋላ የተናገሩት ስለካድሬ ነበር ”ካዴሬ” አሉ ሰውዬው፣ቃሉን ጠበቅ አድርገው፣ ”ካድሬ የሚለውን የኢህአዲግ ቋንቋ መጠቀማችን ያስንቀናል፡፡ ካድሬ የሚለው ቃል ፊታውራሪ፣ዲያቆን ወይም ስልጡን ተብሎ እንዲተካ እጠይቃለሁ።” ጥያቄው በወቅቱ አስቆኝ ስለነበር ምላሽ ይሰጠው ይሆን በሚል ተጠባበቅኩ፣ መድረክ መሪዎቹ ጉዳዩ አላስጨነቃቸውም ወይም ከግምት በታች ሆኖባችው ነው መሰለኝ ቅርጫት ውስጥ ሲወረውሩት ተመለከትኩ“
የረከሰ ፍርድ በመጽሐፉ ገዢ ርዕስነት መመረጡ አይበዛበትም፡፡ አንድን ሃገር እንደ ካስማ ተሸክሞ አስተማማኝ መደላደል ላይ የሚያቆመው የሕግ ልዕልና ነው፡፡ የሕግ ልዕልና በነጠፈበት ሃገር የአገዛዙ መርህ ጉልበት ይሆናል፡፡ በሕግ አራዊት መርህ /Mighty is right/ የተቃኘ ሥርዓት ፍትህን ያጓድላል፣ብይን ያረክሳል፤ በእዚህም ምክንያት ሃገር በውድቀት ተዳፋት ላይ እንድትንደረደር ጥርጊያውን ያመቻቻል፡፡ የረከስ ፍርድ ጭብጥም ከእዚህ ብዙ ፈቀቅ ያለ አይደለም፡፡ በእየዘመኑ ሰለባ የሆኑትን ሰማዕታት እማኝ እያደረገ የውድቀቱን ሸለቆ መጠቆም ዋንኛ ዓላማው ነው፡፡
የረከሰው ፍርድ ትዕይንት በታላቁ ሰማዕት አቡነ ጴጥሮስ ቡራኬውን በእዚህ መልኩ ይጀምራል፡-(ገጽ 75)
“ፊትዎን ለመሸፈን ይፈልጋሉ?” ሲል አንደኛው ገዳይ ጠየቃቸው
“ይህ የአንት ሥራ ነው!” ሲሉ በተረጋጋ መንፈስ መለሱ፡፡ መጀመሪያ በእጃቸው ይዘውት የነበረውን መጽሐፍ ቅዱስ ተሳለሙ፡፡ የያዙትን መስቀል አማትበው ሕዝቡን ባረኩ፡፡ የኪሳቸውን ሰዓት አውጥተው ካዩ በኋላ መልሰው ከተቱት”
ከአቡነ ጴጥሮስ የጀመረን ልክፍት እያንደረደረ ከእዚህ ዘመን ላይ ያደርሰናል፡፡ ደራሲው ለፍርድ መራከስ እንደ እማኝነት ከወሰዳቸው ንጹሓን መካከል የጀኔራል መንግሥቱ ንዋይ የፍርድ ሁኔታ በተለይ አቅጣጫ መታየት ነበረበት፡፡ ጀኔራሉን ለፍርድ መራከስ ዋቢ ለማድረግ የሕግ-መርህን መጣስ የግድ ይኖርበታል፡፡ በአምስት ዓመቱ የፋሽስት ወራራ ላይ በጀግንነት ሲዋደቁ የነበሩት አርበኞች በንጉሱ ባለሟልነት ተፈርጀው አንደዋዛ ጭዳ የሆኑት በጀኔራሉ እጅ ነበር፡፡ ታዲያ ለጠፋው ነፍስ ተመጣጣኝ ብይን መስጠት ምኑ ላይ ፍርድን የሚያርክስው? በአንጻሩ ይህንን ብይን ቸል ማለት ከሕግ መርህ ጋር ፊት ለፊት የሚያላትም፣ የማያመልጡት ደረቅ እውነታ እንደሆነ እሙን ነው፡፡ እዚህ ጋ ለክርክር ከሚጋብዘው የጀኔራል መንግሥት ንዋይ የሞት ፍርድ ይልቅ የጀግናው በላይ ዘለቀ ኢፍትሃዊ ብይን መካተት ቢችል ኖሮ መልካም  ጎኑ የበዛ ይሆን ነበር፡፡ በርሃ ለበርሃ ለእናት ሃገሩ ሲማስን የኖረው ጀግናው በላይ ዘለቀ፣ ከባንዳዎች ቀድሞ ክንዱን እንዲንተራስ የተፈረደበት ታሪካዊ ክስተት ከሁሉም ልቆ ዓይን የሚገባ የሕግ ክሽፈት ነው፡፡
ፀሐፊው የረከሰ ፍርድን የመሰለ ቋጥኝ ቁምነገርን ባነሳበት እጁ የፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያም  ወርቃማ ሐሳቦችን እንደ ጭብጦ ጨብጦ ከአንጀታችን የሚጠጋ ጉርሻ ያቀብለናል፡፡ እስቲ ይህንን ውስጥን የሚበረብር የፕሮፌሰሩን ወርቃማ ሐሳብ ከገጽ 103 ላይ እንቃኝ፡- “ኢትዮጵያዊነት ከጎሰኝነት በላይና ውጭ የሆነ አጠቃላይ ማንነት ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነት የደጋው ብርድና የቆላው ሙቀት የሚገናኙበት፣የደጋው ዝናብ ከቆላው ወንዝ ጋር የተዛመደበት ኃይል ነው። ኢትዮጵያዊነት ለሙሴ፣ለክርስቶስና ለመሐመድ የሚጨሰው እጣን በእርገት መጥቆ የሚደባለቅበት እምነት ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነት በቄጤማ ጉዝጓዝ ላይ የሚታየው መተሳሰብና መፈቃቀር ነው። ኢትዮጵያዊነት የአስተዋይነት፣ የሚዛናዊነትና የጨዋነት ባህርይ ነው፤ ረጅምና ተጽፎ ያላለቀም ታሪክ ነው”
 ደራሲ አለማየሁ ገበየሁ ስሜቱ ስስ የሆነበትን ሥፍራ አንባቢ ላይ ለማጋባት በብርቱ የተውተረተበት ክፍል ይህ የፕሮፌሰሩ ወርቃማ ሐሳቦች ታሪክ ይመስለኛል፡፡ በእርግጥም በፕሮፌሰሩ ወርቃማ ሐሳቦች ላለመነደፍ ፀጉረ ልውጥ፣ ባዕድ፣ሳላቶ፣ባንዳ፣”ፋሺስት” መሆንን ይጠይቃል፡፡     የረከስ ፍርድ ጅማሮ እንጂ መቋጫ አይመስለኝም፡፡ አለማየሁ ገና ብዙ የሚናገራቸው ወይም የሚተነፍሳቸው ቁጭቶች፣ትዝብቶች እና ስላቆች እንዳሉት ከእያንዳንዱ ታሪክ ጀርባ የመሸጉ እውነታዎች ሹክ ይሉናል፡፡ ለአሁኑ ግን እጅ ብንነሳው አይበዛበትም፡፡  

Published in ጥበብ

      ጽልመት በለበሰ እልፍ አዕላፍ የሰው ዘር ላይ እንደ መርግ ለመጫን የሚንደረደር ብይን መስጫ መዶሻ ከመጽሓፉ ልባስ ላይ ታትሟል፡፡ የልባሱ ገጽታን ተመልከተን የሚፈጠርብን ብዥታ የለም። አንዴ ገርመም አድርገን የፍሬ ነገሩ መቋጫን ለመተንበይ ብዙ መራቀቅ አይጠበቅንብም፡፡
መንደርደሪዬ የአለማየሁ ገበየሁ የረከሰ ፍርድ በኢትዮጵያ መጽሐፍን ይመለከታል፡፡ መጽሐፉ በ189 ገጾች  የተቀነበበ ሲሆን በውስጡ ካቀፋቸው አስራ አራት አጫጭር ታሪኮች ፣ መጣጥፎች እና ዘገባዎች የፊትአውራሪነትን ካባ የለበሰው አንሳርማ የተባለው የፋንታሲ አጻጻፍ ስልትን የተከተለ ምናባዊ  ፈጠራ ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ የአጻጻፍ ዘይቤ የጆርጅ ኦርዌልን Animal farmን ያስታውስናል፡፡
አንሳርማ ገና ከጅምሩ ጠንከር ባለ መፈክር ነው የሚቀበለን፡፡
‘ከአሳማዎች አስተዋይ አመራር ጋር ወደ ፊት’
ከእልፍኙ እንደዘለቅን በገጽ 24 ላይ ራዞር የተባለው አሳማ አስገራሚ ዲስኩሩን ይጋብዘናል፡-
“ጓዶች! እንደምታውቁት ሕገ መንግሥታችን የተዋቀረው ሁሉም እንስሳት እኩል ናቸው በተባለው ፍልስፍና ላይ ነው፡፡ ይህ መርህ መቼም ቢሆነ አይሸራረፍም፡፡ ኾኖም ይህን ድፍን ሐሳብ እንደ አትላስ ተሸክሞ ሥራ ማከናወን አይቻልም። ለዚህም ነው ለረጅም ጊዜ ስንሠራ የቆየነው፡፡ የከተማችን ስያሜ፣ባንዲራችንና ብሔራዊ መዝሙራችን እስካሁን የሠራናቸው የማስፈጸሚያ ስልቶቻችን አካላት አድርጎ መውሰድ ይቻላል፡፡ በዋናነት ደግሞ የአፈጻጸሙ መመሪያ “ሁሉም እንሰሳት በመርህ ደረጃ እኩል ናቸው፤ነገር ግን አንዳንድ እንስሳት ከሌሎች ከእኩል በላይ ሊሆኑ ይችላሉ” ተብሎ መደንገጉን ሳበስር በደስታ ነው፡፡”
አንሳርማ እና የጆርጅ ኦርዌል “አኒማል ፋርም” የሚያስተላለፉት ጭብጥ፣ የሚንደረደሩበት መላምት እና የሚደርስቡት ድምዳሜ ኩታገጠም ነው፡፡ አንሳርማም ሆነ አኒማል ፋርም ዙሪያ ጥምጥም አይሄዱም፡፡ በአሳማ ዝርያ የተመሰለን አጓጉል ሰብዕናን በጥበብ ሾተል እየዋጋጉ የተደራሲያንን ንቃት ከከፍታ ላይ ለመስቀል ተፍ ተፍ ይላሉ፡፡ ከአሳማ ዘር ጋር በአንድ ማሕጠን የተኙት ራስ ወዳድ እንደራሴዎች በእዚህ ዓይነቱ የጥበብ አውድ ላይ ሲበለቱ ማየት ለአንባቢው የሚፈጥረው ስሜት የላቀ ነው፡፡
ደራሲው በአንሳርማ ምህዋር ላይ እንድንሽከረከር ምናባዊ መንኮራኮር ፈብርኮልን ነበር፡፡ ግና አመስግነነው ከአፋችን ሳንጨረስ ምናባዊው ጉዞው እክል ገጥሞት ቁልቁል ያምዘገዝገናል። የተከናነብነው የጥበብ ጃኖ ከላያችን ላይ ተገፎ በቅጽበት በቆፈን እንኮማተራለን፡፡
ተዓምረኛው የቅንጅት ምልክት  በሚለው ታሪክ ሥር አቧራ የጠገቡ ችኮ ዘገባዎች የአንሳርማን ሙቀት ተሻምተው ከፊት ለፊታችን ገጭ ይላሉ፡፡ ፀሐፊው የታሪኩ አሰላለፍ ብዙም ግድ የሰጠው አይመስልም። በአንሳርማ እግር የተተካው ታሪክ ፍዝነቱ የበዛ ነው። ጭልጥ ካለ ምናባዊ ፈጠራ ወደ አረጀ አፈጀ ደረቅ ዘገባ በመንደርደራችን የተነሳ በጋመው ስሜታችን ላይ ቀዝቃዛ ውኃ ይቸለሳል፡፡ የመጽሐፉ ገዢ ርዕስ የአንሳርማን እግር ተከታይ ቢሆን ኖሮ ሚዛናዊ ስሜት በመፍጠሩ ረገድ የሚታማ አይሆንም ነበር። አንሳርማ እና የረከሰ ፍርድ ሰም እና ወርቅ ናቸው። አንሳርማ “ስክሪፕት”፣ የረከሰ ፍርድ ተውኔት ነው፡፡ እነዚህ ተደጋጋፊ ታሪኮች እግር በእግር እንዳይከታተሉ የይለፍ ፍቃድ ተነፍገዋል፡፡
ደግነቱ ደራሲውን ብዙም ሳናማው መልሶ ይክሰናል፡፡ በጥበብ ማጀቱ ከቋጠረው ጥሪት ያለ ስስት እያቃመሰን የዳመነውን  ገጽታችንን ለማፍካት ይተጋል፡፡ የግብዣ ማግደርደሪያውን በገጽ 52 ላይ እናገኛለን፡-
“ማስታወሻ ደብተሬን በገለበጥኩ ቁጥር ፊቴ ፈገግ፣ቅጭም ይል ነበር፡፡ ገጹን እንዲህ የሚቀያይረው አስደሳች፣አስገራሚና አሳዛኝ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በጉዳዮቹ ውስጥ ደግሞ መረጃ የሚሰጡ ሰዎችና የሚጠይቁ ጋዜጠኞች አሉ፡፡ በዜና ካበጡ በርካታ መረጃዎች ውስጥ የንባብ ብርሃን ያላገኙትን ጥቂቶቹን መራርጬ እነሆ እንድታነቧቸው ጋበዝኳችሁ፡፡”
በአለፍ ገደም የተቃረሙት እውነታዎች በእርግጥም የባለሙያ እጅ የጎበኛቸው ክሽኖች ናቸው፡፡ አንዳንዴም ፊታችንን ቅጭም እያደረገን አንዳንዴም በፈገግታ እየተደነቃቀፍን ከገበታው እንቋደሳለን፡፡ ገጽ 54 ላይ ይህ ግርምት ተከትቧል፡-
“ቦታው አዲስ አበባ ነው፡፡ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት /መኢአድ/ አጠቃላይ ስብሰባ ጠርቶ በተለያዩ ርዕስ ጉዳዮች ላይ አባላቱ ውይይት እያደረጉ ነው፡፡ አንዳንዴ ከዋና ርዕስ ያፈነገጡ አንዳንድ ጉዳዮች ሳይታሰብ ቦግ ብለው ይወጣሉ፡፡ አንዳንድ አባላት አስተያየት ከሚሰጡበት ዋና ጉዳይ አስቀድመው እንደ አፍ ማሟሻ ይሁን ነገር ማጣፈጫ በስሜት የሚናገሯቸው ቃላት ትኩረት ሳቢና ፈገግታ ጫሪ ናቸው፡፡
አንድ ታሳታፊ እድሉ ከተሰጣቸው በኋላ የተናገሩት ስለካድሬ ነበር ”ካዴሬ” አሉ ሰውዬው፣ቃሉን ጠበቅ አድርገው፣ ”ካድሬ የሚለውን የኢህአዲግ ቋንቋ መጠቀማችን ያስንቀናል፡፡ ካድሬ የሚለው ቃል ፊታውራሪ፣ዲያቆን ወይም ስልጡን ተብሎ እንዲተካ እጠይቃለሁ።” ጥያቄው በወቅቱ አስቆኝ ስለነበር ምላሽ ይሰጠው ይሆን በሚል ተጠባበቅኩ፣ መድረክ መሪዎቹ ጉዳዩ አላስጨነቃቸውም ወይም ከግምት በታች ሆኖባችው ነው መሰለኝ ቅርጫት ውስጥ ሲወረውሩት ተመለከትኩ“
የረከሰ ፍርድ በመጽሐፉ ገዢ ርዕስነት መመረጡ አይበዛበትም፡፡ አንድን ሃገር እንደ ካስማ ተሸክሞ አስተማማኝ መደላደል ላይ የሚያቆመው የሕግ ልዕልና ነው፡፡ የሕግ ልዕልና በነጠፈበት ሃገር የአገዛዙ መርህ ጉልበት ይሆናል፡፡ በሕግ አራዊት መርህ /Mighty is right/ የተቃኘ ሥርዓት ፍትህን ያጓድላል፣ብይን ያረክሳል፤ በእዚህም ምክንያት ሃገር በውድቀት ተዳፋት ላይ እንድትንደረደር ጥርጊያውን ያመቻቻል፡፡ የረከስ ፍርድ ጭብጥም ከእዚህ ብዙ ፈቀቅ ያለ አይደለም፡፡ በእየዘመኑ ሰለባ የሆኑትን ሰማዕታት እማኝ እያደረገ የውድቀቱን ሸለቆ መጠቆም ዋንኛ ዓላማው ነው፡፡
የረከሰው ፍርድ ትዕይንት በታላቁ ሰማዕት አቡነ ጴጥሮስ ቡራኬውን በእዚህ መልኩ ይጀምራል፡-(ገጽ 75)
“ፊትዎን ለመሸፈን ይፈልጋሉ?” ሲል አንደኛው ገዳይ ጠየቃቸው
“ይህ የአንት ሥራ ነው!” ሲሉ በተረጋጋ መንፈስ መለሱ፡፡ መጀመሪያ በእጃቸው ይዘውት የነበረውን መጽሐፍ ቅዱስ ተሳለሙ፡፡ የያዙትን መስቀል አማትበው ሕዝቡን ባረኩ፡፡ የኪሳቸውን ሰዓት አውጥተው ካዩ በኋላ መልሰው ከተቱት”
ከአቡነ ጴጥሮስ የጀመረን ልክፍት እያንደረደረ ከእዚህ ዘመን ላይ ያደርሰናል፡፡ ደራሲው ለፍርድ መራከስ እንደ እማኝነት ከወሰዳቸው ንጹሓን መካከል የጀኔራል መንግሥቱ ንዋይ የፍርድ ሁኔታ በተለይ አቅጣጫ መታየት ነበረበት፡፡ ጀኔራሉን ለፍርድ መራከስ ዋቢ ለማድረግ የሕግ-መርህን መጣስ የግድ ይኖርበታል፡፡ በአምስት ዓመቱ የፋሽስት ወራራ ላይ በጀግንነት ሲዋደቁ የነበሩት አርበኞች በንጉሱ ባለሟልነት ተፈርጀው አንደዋዛ ጭዳ የሆኑት በጀኔራሉ እጅ ነበር፡፡ ታዲያ ለጠፋው ነፍስ ተመጣጣኝ ብይን መስጠት ምኑ ላይ ፍርድን የሚያርክስው? በአንጻሩ ይህንን ብይን ቸል ማለት ከሕግ መርህ ጋር ፊት ለፊት የሚያላትም፣ የማያመልጡት ደረቅ እውነታ እንደሆነ እሙን ነው፡፡ እዚህ ጋ ለክርክር ከሚጋብዘው የጀኔራል መንግሥት ንዋይ የሞት ፍርድ ይልቅ የጀግናው በላይ ዘለቀ ኢፍትሃዊ ብይን መካተት ቢችል ኖሮ መልካም  ጎኑ የበዛ ይሆን ነበር፡፡ በርሃ ለበርሃ ለእናት ሃገሩ ሲማስን የኖረው ጀግናው በላይ ዘለቀ፣ ከባንዳዎች ቀድሞ ክንዱን እንዲንተራስ የተፈረደበት ታሪካዊ ክስተት ከሁሉም ልቆ ዓይን የሚገባ የሕግ ክሽፈት ነው፡፡
ፀሐፊው የረከሰ ፍርድን የመሰለ ቋጥኝ ቁምነገርን ባነሳበት እጁ የፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማሪያም  ወርቃማ ሐሳቦችን እንደ ጭብጦ ጨብጦ ከአንጀታችን የሚጠጋ ጉርሻ ያቀብለናል፡፡ እስቲ ይህንን ውስጥን የሚበረብር የፕሮፌሰሩን ወርቃማ ሐሳብ ከገጽ 103 ላይ እንቃኝ፡- “ኢትዮጵያዊነት ከጎሰኝነት በላይና ውጭ የሆነ አጠቃላይ ማንነት ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነት የደጋው ብርድና የቆላው ሙቀት የሚገናኙበት፣የደጋው ዝናብ ከቆላው ወንዝ ጋር የተዛመደበት ኃይል ነው። ኢትዮጵያዊነት ለሙሴ፣ለክርስቶስና ለመሐመድ የሚጨሰው እጣን በእርገት መጥቆ የሚደባለቅበት እምነት ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነት በቄጤማ ጉዝጓዝ ላይ የሚታየው መተሳሰብና መፈቃቀር ነው። ኢትዮጵያዊነት የአስተዋይነት፣ የሚዛናዊነትና የጨዋነት ባህርይ ነው፤ ረጅምና ተጽፎ ያላለቀም ታሪክ ነው”
 ደራሲ አለማየሁ ገበየሁ ስሜቱ ስስ የሆነበትን ሥፍራ አንባቢ ላይ ለማጋባት በብርቱ የተውተረተበት ክፍል ይህ የፕሮፌሰሩ ወርቃማ ሐሳቦች ታሪክ ይመስለኛል፡፡ በእርግጥም በፕሮፌሰሩ ወርቃማ ሐሳቦች ላለመነደፍ ፀጉረ ልውጥ፣ ባዕድ፣ሳላቶ፣ባንዳ፣”ፋሺስት” መሆንን ይጠይቃል፡፡     የረከስ ፍርድ ጅማሮ እንጂ መቋጫ አይመስለኝም፡፡ አለማየሁ ገና ብዙ የሚናገራቸው ወይም የሚተነፍሳቸው ቁጭቶች፣ትዝብቶች እና ስላቆች እንዳሉት ከእያንዳንዱ ታሪክ ጀርባ የመሸጉ እውነታዎች ሹክ ይሉናል፡፡ ለአሁኑ ግን እጅ ብንነሳው አይበዛበትም፡፡   

Published in ጥበብ

     ምንም የተፈጥሮ ሀብት የሌላቸው እንደ ዱባይ ያሉ አገሮች ሰው ሰራሽ የቱሪስት መስህብ እየሰሩ የጎብኚዎችን ልብ ሲያማልሉ ኢትዮጵያ በተፈጥሮ፣ በሰው ሰራሽና በህዝቦቿ ቱባ ባህል የበለፀገች ብትሆንም አገሪቷም ሆነች ህዝቦቿ ለዘመናት የዚህ ሀብት ተጠቃሚ አለመሆናቸው በርካታ ኢትየጵያውያን የሚቆጩበት ጉዳይ ሆኖ ቆይቷል፡፡
ሰሞኑን ግን እንደ እግር እሳት የሚለበልበውን ቁጭታቸውን የሚያበርድ ዜና ከወደ አውሮፓ ተሰምቷል፡፡ ይኸውም የአውሮፓ ቱሪዝምና ንግድ ም/ቤት ጠቅላላ ጉባኤ ኢትዮጵያን በ2015 የዓለም ምርጥ የቱሪዝም መዳረሻና ተመራጭ የባህላዊ ቱሪዝም መዳረሻ በማለት በሁለት ዘርፎች መምረጡን የባህልና ቱሪዝም ሚ/ር አስታውቋል፡፡
ሚ/ር መስሪያ ቤቱ ሰሞኑን በሰጠው መግለጫ፣ ኢትዮጵያ ከ31 የዓለም አገራት ጋር ተወዳድራ በቀዳሚነት መመረጧና እውቅና ማግኘቷ መንግሥት ለቱሪዝም ኢንዱስትሪ በተለይም ባህላዊ ቱሪዝምን ለማስፋፋት ያለውን ፍላጎትና ቁርጠኝነት ያመለክታል ተብሏል፡፡
መንግሥት በ2006 ዓ.ም የኢትዮጵያ ቱሪዝም ድርጅትን በአዋጅ አቋቁሞ የቱሪዝም መዳረሻዎችን እንዲያለማና የቱሪዝም ገበያውን እንዲመራ አድርጓል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በዚሁ ዓመት በጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራ የቱሪዝም ትራንስፎርሜሽን ም/ቤት አቋቁሞ ለዘርፉ ዕድገት እየሠራ መሆኑ ታውቋል፡፡ ጠቅላይ ሚ/ር ኃይለማርያም ደሳለኝ ለጪስ አልባው ኢንዱስትሪ መበልፀግ የሰጡት ትኩረት በአውሮፓ የቱሪዝምና ንግድ ም/ቤት ጠቅላላ ጉባኤ እውቅና ከማግኘቱም በላይ ከ28 አገራት መሪዎች ጋር ተወዳድረው ግንባር ቀደም የቱሪዝም መሪ በመባል እንዲመረጡ አድርጓቸዋል፡፡ ሽልማታቸውንም በመጪው ሳምንት አርብ እንደሚቀበሉ ተገልጿል፡፡
ኢትዮጵያ ቱሪዝምን ለድህነት ቅነሳ፣ ለስራ ፈጠራ፣ ለዜጎች መተዳደሪያ፣ ለሰላም ግንባታና ለዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትና ለአገር ገፅታ ግንባታ፣ … እንዲውል ማድረጓ እንዳስመረጣት መግለጫው አስታውቋል፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፡፡ በርካታ ብሔር/ብሔረሰቦችን አቅፋ መያዟ፣ የአገሪቷ መልክአምድራዊ አቀማመጥ በጣም ውብና አስደናቂ መሆን፣ በተራራማ አቀማመጧ የአፍሪካ ጣሪያ፣ በበርካታ ወንዞችና ድርጅቶቿ የአፍሪካ የውሃ ማማ መባሏ፣ ህዝቦቿ ለዘመናት ያካበቱት የየራሳቸው ድንቅ ባህልና የባህል መገለጫዎች፣ ባለፉት 10 ዓመታት የባህልና የተፈጥሮ መስህቦቿን ሀብት ለዓለም የቱሪስት ገበያ በማስተዋወቅ ከዘርፉ በሚገኝ ሀብት ህዝቦቿን ተጠቃሚ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት ማድረጓ፣ በ2015 ምርጥ የቱሪስት መዳረሻ ለመሆን እንዳበቃት ተነግሯል፡፡  
እስካሁን ድረስ ኢትዮጵያን በሰው ዘር መገኛነት የሚቀድማት የለም.፡፡ ከማንኛውም አገር የበለጠ በርካታ የቅድመ ታሪክና የሰው ዘር መገኛ መካነ ቅርስ ስላላት ጥናትና ምርምር ከሚደረግባቸው አገሮች አንዷና ተመራጭ ናት፡፡ ከ3 ሚሊዮን በላይ ዕድሜ ያስቆጠሩትን የሉሲ  ወይም ድንቅነሽና ሌሎች ቅሪተ አካላት፣ የጎና ጥንታዊ ድንጋይ መካነ ቅርስ ቦታዎች፣ የታችኛው ኦሞ ሸለቆ ታሪካዊ ግብረ ህንፃዎች፣ ሰማይ ጠቀስ ሀውልቶች፣ ዘመናት ያስቆጠሩ የሦስቱ ሃይማኖቶች የታሪክ አሻራዎች (ፍልፍል ቤተክርስቲያናት፣ ጥንታዊ መስጊዶችና ቤተ - እምነቶች) የሃይማኖት አባቶች የመቃብር ቤቶች፣ ለምርጫ ያበቋት ሀብቶቿ ናቸው፡፡
ከዚህም በተጨማሪ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርሶች ባለቤት መሆኗም ተገልጿል፡፡ በሚዳሰሱ ቅርሶች የአክሱም ሀውልቶች፣ የጎንደር አብያተ መንግስታት፣ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፣ የጢያ ትክል ድንጋይ፣ የሀረሩ ጀጎል ግንብ፣ የኮንሶ መልክአ ምድር፣ የሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ፣ የታችኛው አዋሽና የታችኛው ኦሞ ሸለቆዎች በዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ ሲሆን፣ ድሬ ሼክ ሁሴን ሆልቃ ሶፍ ኡመር፣ የጌዴኦ ጥምር ግብርና መልክአ ምድር፣ የመልካ ቁንጡሬ ቅድመ ታሪክ መካነ ቅርስና የባሌ ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ በዓለም ቅርስነት መዝገብ ውስጥ ለመካተት ተራ እየጠበቁ ነው፡፡
በማይዳሰሱ ቅርሶች ደግሞ የመስቀል በዓል በዓለም የውክልና መዝገብ (ዎርልድ ሬፕሬዘንታቲቭ ሊስት) የተመዘገበ ሲሆን የሲዳማ ዘመን መለወጫ ጨንበላላ በዓልና የገዳ ስርዓት በዓለም የውክልና መዝገብ እንዲካተቱ በቅርቡ ለዩኔስኮ እንደምትልክ ታውቋል፡፡
12 ጥንታዊ ጽሑፎችና መዛግብት በዓለም ሜሞሪ ዝርዝር ውስጥ የተመዘገቡ ሲሆን በቅርቡም ሁለት ጥንታዊ ጽሑፎች መላኳ ተገልጿል፡፡ በጥብቅ የተፈጥሮ አካባቢዎች ከሽካ፣ ከካፋና ያዩ በተጨማሪ የጣና ሐይቅ አካባቢም ባለፈው ወር ተመዝግቧል፡፡
ከሁሉም በላይ ኢትዮጵያን ምርጥና ተመራጭ የቱሪስት መዳረሻ ሆና እንድትመረጥ ያደረጋት ሰላምና ፀጥታ ማስከበሯና ለቱሪስቶች ደህንነት ምቹ መሆኗ እንደሆነ መግለጫው አመልክቷል፡፡