“How Successful People Think” በሚል ርዕስ በዶ/ር ጆን ማክስዌል ተፅፎ፣ በአባተ መንግስቱ የተተረጎመው “የአሸናፊነት መንገዶች” የተሰኘ መፅሀፍ ባለፈው ሳምንት ለአንባቢያን ደርሷል፡፡ መፅሀፉ እንዴት ወደ አሸናፊነትና ስኬት እንደሚደረስና የመድረሻ መንገዱን የሚያመለክቱ ቁልፍ ነጥቦች የተነሱበት ሲሆን በተለይም በትኩረት ስለማሰብ፣ የፈጠራ አስተሳሰብን ስለመግራትና ስልታዊ አስተሳሰብን ስለመቃኘት በስፋት ይተነትናል፡፡ በ11 ርዕስ ጉዳዮች ላይ ትኩረት ያደረገው መፅሀፉ፤ በ168 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን በ46 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ በተያያዘ ዜና በዮሐንስ በላይ የተደረሰው “ሃመልማል” የተሰኘ ልብወለድ መፅሀፍ አንባቢያን እጅ ደርሷል፡፡ መቼቱን ደሴና ኮምበልቻ ላይ ያደረገው ድርሰቱ፤ አዝናኝ የፍቅርና የህይወት ታሪክን ነው ተብሏል፡፡ 57 ገፆች ያሉት የዮሐንስ በላይ መፅሀፍ፤ በ25 ብር ገበያ ላይ ውሏል፡፡

የባለቅኔ ፀጋዬ ገ/መድህን ሥራዎችን የሚቃኘውና “ምሥጢረኛው ባለቅኔ” በሚል ርዕስ በደራሲ ሚካኤል ሽፈራው ተዘጋጅቶ በ1996 ዓ.ም ለአንባቢያን ቀርቦ የነበረው መጽሐፍ፤ በ10ኛ ዓመቱ ለሁለተኛ ጊዜ ታተመ፡፡ ደራሲው ለመጽሐፉ ሰፊ የአርትኦት ሥራ ማከናወናቸውንና አዳዲስ መረጃዎችን ማካተታቸውን በመግቢያው ላይ አመልክተዋል፡፡ 365 ገፆች ያሉት መጽሐፉ፤ በ80 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

ጋዜጠኛ፣ ደራሲና ዓለም አቀፍ የሰላም አምባሳደር በሆነው ወጣት መኮንን ሞገሴ የተዘጋጀው “ከልካይ የሌለው ስጥ” የተሰኘ መፅሀፍ የፊታችን ሰኞ በብሄራዊ ቴአትር ይመረቃል፡፡ መፅሀፉ በዩኒቨርሲቲ ሴት ተማሪዎች የስነ-ልቦና ዝቅጠት ላይ ያተኩራል የተባለ ሲሆን ፀሐፊው በስድስት ወራት የመስክ ቆይታው በአዲስ አበባ፣ ሃዋሳ፣ ዲላ፣ ሐገረ-ማርያም፣ ያቤሎ፣ ኢትዮጵያ ሞያሌ፣ ኬኒያ ሞያሌ እና ኬንያ ጋንቦ ድረስ በመሄድ በጎዳና ተዳዳሪነት፣ በተሸካሚነት እንዲሁም በአስተናጋጅነት እየሰራ የታዘባቸውን የከተበበት እንደሆነ ታውቋል፡፡ በእሁል ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን አስተባባሪነት የሚመረቀው መፅሀፉ፤ የደራሲው ሁለተኛ ስራ ሲሆን ከዚህ ቀደም “የአስተናጋጁ ገፆች ቅፅ 1” የተሰኘ መፅሀፍ ለንባብ ማብቃቱ ታውቋል፡፡

በሰአሊና ደራሲ ገዛኸኝ ዲኖ የተፃፈው “በቃ እንሂድ” የተሰኘ ልብወለድ መፅሀፍ የፊታችን ማክሰኞ በሩሲያ የሳይንስና የባህል አዳራሽ ከቀኑ 10፡00 ሰዓት ጀምሮ ይመረቃል፡፡ 460 ገፅ ያለውና መቼቱን ኢትዮጵያና ፈረንሳይ ላይ ያደረገው መፅሃፉ፤ በአንድ ሰዓሊ ህይወት ላይ ያጠነጥናል፡፡ በምርቃት ስነ-ስርዓቱ እለት ደራሲያንና ሌሎች እንግዶች የሚገኙ ሲሆን በመፅሀፉ ዙሪያ ውይይት ይካሄዳልም ተብሏል፡ መፅሐፉ በ70 ብር ከ85 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡ የመፅሃፉ፤ ደራሲ ሰዓሊ ገዛኸኝ ዲኖ ለ19 ዓመታት በፈረንሳይ አገር እንደኖረ ታውቋል፡፡

በዘረሰናይ መሃሪ ተፅፎ የተዘጋጀውና በእውቋ የፊልም ኮከብ ተዋናይ አንጀሊና ጆሊ ፕሮዲዩስ የተደረገው “ድፍረት” ፊልም የፊታችን ሐሙስ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በአሜሪካ ለመጀመሪያ ጊዜ በተመልካች ምርጫ አሸንፎ ለሽልማት የበቃውና በአንዲት ኢትዮጵያዊት የገጠር ታዳጊ እውነተኛ የጠለፋ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው ፊልሙ፤ በ64ኛው የበርሊን ዓለም አቀፍ ፊልም ፌስቲቫል ላይ ተሸላሚ ሆኗል፡፡ ዓለም አቀፍ አድናቆት የተቸረው ይሄ ፊልም በሚቀጥለው ሃሙስ የመንግስት ኃላፊዎች፣ የፊልሙ ደራሲና ዳይሬክተር ዘረሰናይ መሃሪና በፊልሙ ላይ የተሳተፉት ተዋንያንና እንዲሁም ታሪኳ በፊልሙ የተካተተው የህግ ባለሙያዋ መዓዛ አሸናፊ በተገኘችበት እንደሚመረቅ የፕሮግራሙ አዘጋጅ “ሃይሌ ፒክቸርስ” ለአዲስ አድማስ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡

  •  ከትኬት ሽያጭ ቢያንስ 5 ሚሊዮን ብር እንደተገኘ ተገምቷል *
  • “ኮንሰርት” የሚወዱ “የእጅ አመለኞች” አስቸግረው ነበር

ከወራት በፊት ሊካሄድ ታቅዶ የነበረው “ሬጌ ዳንሶል ኢን ኢትዮጵያ ቁጥር 1” የሙዚቃ ኮንሰርት የተሰረዘው ከቴዲ አፍሮ ኮንሰርት ጋር በመገጣጠሙ እንደነበር አዘጋጁ “አውሮራ ኤቨንት ኦርጋናይዘርስ” መግለጹ ይታወሳል፡፡ የኮንሰርቱ ተጋባዥ ከያኒ ጃማይካዊው ቢዚ ሲግናል ለሸገር ሬዲዮ በሰጠው ቃለምልልስ ደግሞ፤ “ኮንሰርቱ የተሰረዘው በተለያዩ ምክንያቶች በተከሰቱ መዘግየቶች ነው” ብሎ ነበር፡፡ የሆነ ሆኖ “ለሁሉም ጊዜ አለው” እንዲሉ፣ ኮንሰርቱ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ በሚሊኒየም አዳራሽ በርካታ ታዳሚያን በተገኙበት ተካሂዷል፡፡ የምሽቱ ድባብ ከምሽቱ 2፡00 ላይ የተጀመረው የሙዚቃ ኮንሰርቱ፤ በአገራችን የሬጌ ሙዚቃ አቀንቃኞችና በዲጄ እየተሟሟቀ የዘለቀ ሲሆን ራስ ጃኒ፣ ሲዲኒ ሳልመን፣ ጃሉድ አወል፣ ሃይሌ ሩትስ እና ጆኒ ራጋ ማራኪ ሥራዎቻቸውን አቅርበዋል፡፡

በየመሃሉ በዲጄ ባባ ትንፋሽ እያገኙ መድረኩን ያደመቁት ኢትዮጵያዊ ድምፃዊያን፤ በታዳሚው ዘንድ ከፍተኛ አድናቆትን አግኝተዋል፡፡ መድረኩ በጥሩ ሁኔታ ተዘጋጅቷል፤ የላይትና የድምፁ ቅንብር እንከን የለሽ ነበር፡፡ ኮንሰርቱ ተጀምሮ እስከሚያልቅ አንድም የድምፅ መቆራረጥና መረበሽ አላጋጠመም፡፡ ድምፃዊያኑ ለኮንሰርቱ በቂ ዝግጅት ለማድረጋቸው በመድረክ ያሳዩት ጥንካሬና ብቃት ምስክር ነው፡፡ ራስ ጃኒ የምሽቱ ምርጥ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ጃሉድ “የገጠር ልጅ ነኝ”፣ “አሻበል ያሆ”፣ የእርግብ አሞራ እና ሌሎችንም ስራዎቹን በጥሩ ሁኔታ በመጫወት ታዳሚውን የማረከ ሲሆን ሃይሌ ሩትስ በበኩሉ፤ “ባዶ ነበር”፣ “እርጅና መጣና” በተሰኙ ታዋቂ ዘፈኖቹ ተመልካቹን አዝናንቷል፡፡ ጆኒ ራጋም አነቃቂ ምሽት ለመፍጠር ችሏል፡፡ ጆኒ ራጋና ሃይሌ ሩትስ በጋራ ተቀናጅተው ያቀረቡት ሥራም ልዩ አድናቆት የተቸረው ነበር፡፡ በየመሃሉ ዲጄ ባባ መድረኩን በሙዚቃ እያደመቀ፣ አርቲስቶቹም ትንፋሽ እየሰበሰቡ፣ ታዳሚውም ልቡ እስኪወልቅ እየጨፈረና እየዘለለ ጊዜው ወደ አምስት ሰዓት ነጐደ፡፡

የዕለቱ “ሰርፕራይዝ” መድረኩን በጥሩ ሁኔታ በመምራት የተሳካለት ጋዜጠኛ አንዷለም ተስፋዬ፤ በኮንሰርቱ መጀመሪያ ላይ “ሰርፕራይዝ” እንዳለ በመግለጽ የታዳሚውን ልብ አንጠልጥሎት ነበር፡፡ እናም የመድረኩ መብራት ደብዝዞ፤አይን የማያጨልም ድባብ ተፈጠረ፡፡ ሰፋፊ ኮፍያ ያደረጉ ሰዎች ደንገዝገዝ ባለው ድባብ ውስጥ እየሮጡ ወደ መድረኩ በመግባት ቦታ ቦታቸውን ያዙ፡፡ ታዳሚው ለ“ሰርፕራይዙ” ጓጉቶ ነበር፡፡ የመድረኩ መብራት ፏ ብሎ በራ፡፡ “ሰርፕራይዟ” ዘፋኝ፤ ነጭ ብልጭልጭ ቲ-ሸርትና ነጭ ቁምጣ ለብሳ ብቅ አለች፡፡ ጭብጨባና ፉጨቱ ቀለጠ፡፡ ድምጻዊት ቤቲ ጂ. “ከአንተ አይበልጥም” የሚለው ዘፈኗን በዳንስ ቡድኗ ታጅባ፣ አብራ እየተውረገረገች አስነካችው፡፡ እየዘፈነችና እየጨፈረች ታዳሚውን አስጨፈረችው፡፡ ሁለተኛ ዘፈኗም ቀጠለ፡፡ በጣም ግሩም አቀራረብ ነበር ያሳየችው፡፡ ሥራዋን ጨርሳ ከመድረክ ስትወርድም በህዝቡ አድናቆትና ሆታ ተሸኝታለች፡፡ የታዳሚውን ልብ የነካ ስራ “እኔ የፕሮግራሙ አዘጋጅ ሆኜ እንኳን አላወቅሁም፤ በጣም የተገረምኩበትና የተደነቅሁበት ጉዳይ ነው” ይላል፤የ“አውሮራ ኤቨንትስ ኦርጋናይዘርስ” ዋና ስራ አስኪያጅ ሸዊት ቢተው፡፡ ቤቲ ጂ.፣ ጃሉድ አወል፣ ሃይሌ ሩትስ እና አንድ ፊቱ አዲስ የሆነ አርቲስት ወደ መድረክ ወጡና ማንም ያልጠበቀውን ዘፈን መዝፈን ጀመሩ፡ “ነገን ላያት እጓጓለሁ” በማለት፡፡

ይሄን ጊዜ ታዳሚው መጮህ፣ ማልቀስና ማፏጨት ያዘ፡፡ በድንገተኛው ዘፈን አዳራሹ ተደበላለቀ፡፡ ከአመት በፊት በድንገት ህይወቱ ያለፈውን የሬጌውን አቀንቃኝ ድምፃዊ ኢዮብ መኮንን ለመዘከር ታስቦ የቀረበው ሙዚቃ የመላ ታዳሚውን ልብ የነካ ነበር፡፡ በመሃል “ወይኔ እዮቤ ውውው…” በማለት ጩኸቷን ያቀለጠችው አንዲት ወጣት ታዳሚ፤እንባዋ በጉንጯ እየወረደ ደረቷን መድቃት ጀመረች፡፡ ጓደኞቿ ተረጋጊ እያሉ ቢያፅናኗትም አልቻለችም፡፡ “እዮቤን በጣም ነው የማደንቀው፤ አሟሟቱም በጣም ያሳዝናል” እያለች ማልቀሷን ቀጠለች፡፡ የብዙሃኑ ታዳሚ ጩኸት፤ ፉጨትና ዝላይማ በቃላት ለመግለጽ አዳጋች ነው፡፡ “ነገን ላያት እጓጓለሁ” ቀጠለ፡፡ አርቲስቶቹ በጣም ያምሩ ነበር፤የሙያ አጋራቸውን የዘከሩበት መንገድም አንጀት ይበላል፡፡ “ይህንን ሃሳብ ያፈለቁት ዝግጅቱን ከእኛ ጋር በአጋርነት የሰሩት የሲግማ ኢንተርቴይንመንት የስራ ባልደረባ ብሩክ እና የአውሮራ ማኔጅመንት አባል ዳዊት ናቸው” ይላል ሸዊት፡፡

ያረፈደው የክብር እንግዳ እኩለ ሌሊት አለፈ፡፡ የእለቱ የክብር እንግዳ ብቅ አላለም፡፡ ዲጄ ባባ የመሸጋገሪያውን ሙዚቃ እያጫወተ 7፡45 ሆነ፡፡ የመድረኩ አጋፋሪ አንዷለም ተስፋዬ ብቅ አለ፡፡ “አሁን በጉጉት የምትጠብቁት እንቁ ድምፃዊ ቢዚ ሲግናል ወደ መድረክ ይመጣል” ሲል አዳራሹ በጩኸት ተሞላ፡፡ ከስንት ጥበቃ እና ጉጉት በኋላ ቢዚ ሲግናል ወደ መድረክ ሲመጣ አዳራሹ ይበልጥ ተናጋ፡፡ ዳልቻ ኮት በነጭ ሸሚዝና ጠቆር ባለ ግራጫ ሱሪ ያደረገው ቢዚ ሲግናል፤ ነጭ ፍሬም ያለው ጥቁር መነፅር ፊቱ ላይ ሰክቶ ለታዳሚው ሰላምታ ሰጠ፡፡ የእሱን ዘፈን ለመስማት ዝግጁ መሆን አለመሆናችንን ጠየቀ፤ “Are you feeling good?” (በጥሩ ስሜት ውስጥ ናችሁ እንደማለት) ታዳሚው በፉጨት እና በጭብጨባ ምላሽ ሰጠ፡፡ በዚህ ምሽት ከዚህ ውብ ህዝብ ጋር በመገናኘቱ የተሰማውን ደስታ አርቲስቱ ገለፀ፡፡ በግምት በ20ዎቹ አጋማሽ ዕድሜ ላይ የሚገኘው ቢዚ ሲግናል፤ እንደብዙዎቹ የሬጌ ሙዚቀኞች ፀጉሩ ድሬድ አይደለም፡፡

ምንም እንኳ በዘፋኝነት ይበልጥ የታወቀው “One more night” የተሰኘውን የፊል ኮሊንሰን ቀደምት ስራ ሪሚክስ አድርጎ ከተጫወተ በኋላ ቢሆንም በርካታ የራሱን ስራዎችም አበርክቷል፡፡ ቢዚ ሲግናል ወደ መድረክ የመጣው ታዳሚው በጭፈራ ጉልበቱን ከጨረሰ በኋላ ነበር፡፡ በየመሃሉ “ቢዩቲፉል ሌዲስ” እያለ ኢትዮጵያውያን ሴቶችን በማድነቅ ማቀንቀኑን ቀጠለ፡፡ አጠገቤ የነበሩ በቡድን የታደሙ ሰዎች “በቃ ያቺን ዋን ሞር ናይት ይዝፈናትና እንሂድ” ሲሉ ሰማኋቸው፡፡ እርሱ ግን አውቆም ይሁን ሳያውቅ ዘፈኗን ወደ መጨረሻ ላይ አደረጋት፡፡ ሲግናል እስከ ሌሊቱ 9፡41 ድረስ መድረክ ላይ ነበር፡፡ ታዳሚው ግን ከቢዚ ሲግናል ይልቅ በኢትዮጵያዊያን አርቲስቶች ይበልጥ መደሰቱን ታዝቤአለሁ፡፡ የኮንሰርቱ አንዳንድ እንከኖች በምሽቱ ድራፍትና ሃሺሽ እኩል ሲጠጡ አመሹ ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ ሀሺሽ በየደቂቃውና በየቅርብ ርቀቱ ይጨሳል፤ እንደጉድ ይጦዛል፡፡ ለሽታው ባዕድ የሆነ ያጥወለውለዋል፡፡ ያስመለሳቸውም ነበሩ፡፡ አጠገቤ የነበረ አንድ ታዋቂ አርቲስት፣ ሃሺሽ ከሚያጨስ አንድ ወጣት ጋር አንገት ለአንገት ሲተናነቅ አይቻለሁ- “ሌላ ቦታ ሄደህ አጭስ” በሚል፡፡ በርካታ ኪስ አውላቂዎችም (ሌቦች) አሰላለፋቸውን አሳምረው ነበር፡፡

ቦርሳዎች፣ ሞባይል ስልኮች፣ የኪስ ቦርሳዎችና ሌሎች ንብረቶች ለመንታፊዎች ሲሳይ ሆነው አምሽተዋል፡፡ አንድ የውጭ ዜጋ “ዋሌቴን ተሰርቄአለሁ፤ ውስጡ ፓስፖርት አለው፤ እባካችሁ እዚሁ እንዳልቀር ፓስፖርቱን እንኳን መልሱልኝ” የሚል መልዕክት በመድረክ አጋፋሪው አስነግሯል፡፡ ባለረጃጅም ተረከዝ ጫማዎችን የተጫሙ ሴቶች እግራቸውን ሲደክማቸው ጫማቸውንና ቦርሳቸውን መሬት ቁጭ አድርገው ሲጨፍሩ የሌባ ሰለባ ሆነዋል፡፡ አንዲት ወጣት “ሌላው ቢቀር ጫማዬን እንኳን ባገኝ---” በማለት እንባዋ እንደጎርፍ እየፈሰሰ፣በታዳሚው ስር በመሽሎክሎክ ጫማዋን ስትፈልግ አስተውያለሁ፡፡ የ“አውሮራ ኤቨንትስ ኦርጋናይዘርስ” ዋና ሥራ አስኪያጅ ሸዊት ቢተው ስለስርቆቱ ጠይቀነው ሲመልስ፤ “የእኛ ኮንሰርት የመጀመሪያ ከማይመስልባቸውና ከሚለይባቸው ጉዳዮች መካከል በምሽቱ ከካራማራ ፖሊስ ጋር በመተባበር አዳራሽ ውስጥ ሆነው የሰው ንብረት የሰረቁ ሌቦችን ይዘን ሞባይል፣ ቦርሳ፣ ፓስፖርትና ሌሎች ንብረቶችን ለባለቤቶቹ ማስመለሳችን ነው” ብሏል፡፡ ከተሰረቁት እቃዎች አብዛኞቹ ለባለቤቶቹ እንደተመለሱና አንድ ሁለት ሰዎች ብቻ እቃቸውን ማግኘት እንዳልቻሉ ሸዊት ተናግሯል፡፡ ኮንሰርቱን ከ10 እስከ 12ሺህ የሚደርሱ ሰዎች እንደታደሙት ከዚህም ውስጥ 2ሺህ ያህሉ በተጋባዥነት እንደገቡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከትኬት ገቢም ቢያንስ 5 ሚሊዮን ብር ገደማ እንደተገኘ ተገምቷል፡፡

Published in ጥበብ

         አልበም ሰርቶ ማጠናቀቅ አምጦ ልጅ የመውለድ ያህል ከባድ ነው ይባላል፡፡ የዚህ አልበም ምጥና ውልደት እንዴት ነበር? እውነት ነው፤ በጣም አስቸጋሪ ሂደትን ማለፍ ይጠይቃል፡፡ እኔም ይህን አልበም እዚህ ለማድረስ ላለፉት ስድስት ዓመታት ስለፋ ቆይቻለሁ፡፡ አሜሪካ ለኮንሰርት በቆየሁበትም ሆነ ለሌላ ስራ ውጭ በነበርኩባቸው ጊዜያት ሁሉ ከአልበም ስራው ላይ አልተለየሁም፡፡

የተለያዩ የአሜሪካ ስቱዲዮዎች ውስጥ ገብቻለሁ፡፡ ለምሳሌ እንደ ሳንዲያጎ፣ ዲሲና ኒውዮርክ በሚገኙ ስቱዲዮዎች ገብቼ ነበር፡፡ የአልበሙ ስራ የተጀመረው አሜሪካ ነው፤ እዚያው እያለሁ ዜማዎችን እሰራ ነበር፡፡ እናም የሙዚቃው ሂደት ውስጥ እጅግ ከባድ እና ፈታኝ ሁኔታዎችን አልፌያለሁ፡፡ ብዙ ወጪ፣ ብዙ ድካምና ጊዜ ፈጅቷል፡፡ እስቲ በጣም ፈታኝ የሆኑብህን ነገሮች ግለፅልኝ? እኛ አገር የድምፃዊያን ፈተና በአብዛኛው የሙዚቀኞች ጉዳይ ነው፡፡ ለምሳሌ የውጭውን አገር ልምድ ብነግርሽ፣ አንድ አልበም ለመስራት ከኩባንያ ጋር ነው ስምምነት የምታደርጊው፡፡ የምትከፍይውም በሰዓት ስለሆነ ጉዳዩን ዋና ስራ አድርገው ነው የሚይዙት፡፡ እዚህ አገር ያሉ ሙዚቀኞችን ስትመለከቺ፣ አንቺ ዛሬ ይህንን ስራ እሰራለሁ፤በዚህ ሰዓት ይሄኛውን እጨርሳለሁ ብለሽ እነሱ ጋር ስትሄጂ “ዛሬ ሙዴ አልመጣም” ይሉሻል፡፡ ሙዳቸው ካልመጣ አይሰሩልሽም፡፡ እዚህ አገር “ሙድ” የሚባል እንደ ባህል የተያዘ ጉዳይ አለ፡፡

በዚህ የተነሳ ያሰብሽውን ሳታሳኪ፣ ያቀድሽውንም ሰዓት ሳትጠቀሚበት ብክነት ውስጥ ትገቢያለሽ፡፡ ይህ የኢትዮጵያ ድምፃዊያን ከፍተኛ ፈተናና ራስ ምታት ነው፡፡ ድምፃዊያንን ብታነጋግሪ ይህንኑ ይነግሩሻል፡፡ ከዚህ ቀደም ሲያማርሩ ሰምተሽም ይሆናል፡፡ ይሄ ግን በሁሉም ሙዚቀኞች ዘንድ የሚስተዋል ነው ማለት አይደለም፡፡ በሌላ በኩል ይሄ “ሙድ” የሚሉት ጉዳይ፣ አንዳንዴ ትክክል ነው ትያለሽ፡፡ በጣም አሪፍ ስራ የሚሰሩልሽ “ሙዳቸው” በመጣ ሰዓት ነው፡፡ ምክንያቱም ሙዚቃ መዝናኛ እንደመሆኑ መጠን የሙዚቀኞቹ ስሜት ወሳኝ ነው፤ ነገር ግን ለድምፃውያኑ ፈታኝ ነው፡፡ ይህን ጉዳይ ያነሳሁት ሲበዛ ስለሚከብድ ነው እንጂ ከ“ሙድ” ውጭ ሆነው ይስሩ ማለቴ አይደለም፡፡ በገንዘብ ረገድ እግዚአብሔር ይመስገን ተቸግሬ አላውቅም፤ በተጓዳኝ ሌሎች ስራዎችንና ኮንሰርቶችን ስለምሰራ፣በገንዘብ እጥረት የአልበሙ ስራ ተስተጓግሎብኝ አያውቅም፤ ነገር ግን ይህን ሁሉ ውጣ ውረድ አልፈሽ ስራውን ካጠናቀቅሽ በኋላ ፕሮዱዩሰሮች (አሳታሚዎች) ጋ ሌላ እንቅፋት ይገጥምሻል፡፡ ምን አይነት እንቅፋት? እዚህ አገር በሙዚቃው ኢንዱስትሪ ለረጅም ጊዜ የቆዩና ትልልቅ የምትያቸው ፕሮዱዩሰሮች የልምድ ስራ እንጂ ፕሮፌሽናል ስራ አይሰሩም፡፡

ስም መጥቀስ ባልፈልግም ትልልቅ የምንላቸው ሙዚቃ ቤቶች፣ አንድ ድምፃዊ ደክሞ ለፍቶ ጥሩ ሚክሲንግ አሰርቶ፣ ማስተሪንጉን ጨርሶ ሊያሰማቸው ሲሄድ በጣም ትንሽ በሆነች ቴሌቪዥንና በአንድ ስፒከር ብቻ ይሰሙታል፡፡ ይሄ ለእኔ ፕሮፌሽናል አሰራር አይደለም፡፡ እንግዲህ እንዲህ የሚያደርጉት አሉ የሚባሉና ትልልቅ የምትያቸው ሙዚቃ ቤቶች ናቸው፡፡ የዚህ አገር የሙዚቃ ኢንዱስትሪ በብዙ መልኩ በችግር የተከበበ ነው፡፡ እነሱ የሚከፍሉት ገንዘብ ብዙ ላይሆን ይችላል፤ ነገር ግን አልበምሽ አድማጭ ጋ እንዲደርስ ጓጉተሸ ወደእነሱ ስትሄጂ እንደዚህ አይነት ችግሮች ይገጥሙሻል፡፡ አንድም የሙዚቃውን ኢንዱስትሪ የገደሉት እነዚህ በልምድ ብቻ የሚሰሩ ሙዚቃ ቤቶች ናቸው፡፡ በአሜሪካ የተለያዩ ስቱዲዮዎች ገብተህ አሰራራቸውን አይተሃል፡፡ እስኪ የታዘብከውን አካፍለን--- የሌላውን አገር ልምድ ስንመለከት፤ ሙዚቃ የሚያቀናብረው ሌላ ሰው ነው፣ ድምፁን የሚቀዳው ሌላ ሰው ነው፣ ማስተሪንግ የሚሰራውም እንዲሁ ሌላ ነው፡፡ በእያንዳንዷ ዘርፍ ውስጥ ስፔሻላይዝ አድርገው ነው የሚሰሩት፡፡

ወደ እኛ አገር ስትመጪ፣ ከሙያተኞች እጥረት የተነሳ እነዚህን ስራዎች የሚሰራቸው አንድ ሰው ነው፡፡ በአሳታሚ ደረጃ ያየሽ እንደሆነ፣ ከአንድ ኩባንያ ጋር ለአምስት ዓመት ይፈራረማሉ፡፡ በአምስት ዓመቱ ውስጥ ማግኘት የሚገባቸውን ነገር ሁሉ ያገኛሉ፡፡ ለምሳሌ ኮንሰርት ይዘጋጃል፣ መኪና ካስፈለገው ሁለት ሶስት መኪና ይዘጋጅለታል፣ በቃ የዚያን ሰው ስራ ኩባንያው ፕሮፌሽናል በሆኑ ሰራተኞቹ ያከናውነዋል፡፡ ሰራተኞቹ በየሙዚቃው ዘርፍ የተማሩና በቂ እውቀት ያላቸው ናቸው፡፡ እዚህ አገር አብዛኛው በልምድ ነው የሚሰራው፡፡ ይሄ ደግሞ ኢንዱስትሪውን ገድሎታል፡፡ ግን እኮ አብዛኛው አድማጭና በሙዚቃው ጠለቅ ያለ እውቀት ያላቸው ሰዎች፣ ለሙዚቃው መዳከም ድምፃውያንን ተጠያቂ ያደርጋሉ… በምን መልኩ? በአሁኑ ወቅት ያሉ አብዛኞቹ ድምፃዊያን አዳዲስ ፈጠራዎች ላይ ከማተኮር ይልቅ በቀደምት ድምፃዊያን በቅጡ የተዘፈኑትን መልሶ በመዝፈንና የበፊት ይዞታቸውን በማበላሸት ለሙዚቃ ኢንዱስትሪው መውደቅ አስተዋጽኦ አበርክተዋል በሚል ይወቅሳሉ፡፡ በዚህ ትስማማለህ? በመሰረቱ ለሙዚቃው ኢንዱስትሪ መውደቅ ተጠያቂዎቹ ሙዚቃ ቤቶች ብቻ ናቸው አላልኩም፡፡ በሙዚቃ ሥራ ውስጥ ስለሚገጥሙ ፈተናዎች ስናወራ፣ ከችግሮቹ መካከል አንዱ መሆናቸውን ለማሳየት ነው የሞከርኩት፡፡ እንዳልሽው እኛም ጋ ችግር ሊኖር ይችላል፡፡

አሁን ላነሳሽው ጥያቄ ግን እንደምታውቂው እኔ ድምፃዊ ብቻ አይደለሁም፤ ጋዜጠኛም ነኝ፡፡ በጋዜጠኝነቴ ከተለያዩ የሙዚቃ ባለሙያዎች ጋር ቃለ-ምልልስ በማደርግበት ጊዜ እንደሚነግሩኝ፣ የቆዩ ሙዚቃዎችን አድሶ መዝፈን አሁን የመጣ ፋሽን ሳይሆን ቀደም ሲልም የነበረ ነው፡፡ ለምሳሌ እነ ሙሉቀን መለሰ ሲመጡ፣ የራሳቸውን ዘፈን ከማውጣታቸው በፊት የቀደምት ዘፋኞችን ሙዚቃዎች ነበር የሚጫወቱት፡፡ የሆነ ትውልድ ወደ ሙዚቃው ሲመጣ፣ የቀደሙትን ዘፈኖች እየተጨዋተ ወደ አዲስ ስራ ይገባል፡፡ ስለዚህ በዚህ ዘመን የመጣ ሳይሆን ድሮም የነበረ ነው ልልሽ ፈልጌ ነው፡፡ ሆኖም በሙዚቃ ኢንዱስትሪው የሚታየው ችግር የአርቲስቱ ነው፣ የሙዚቃ ቤቱ ነው፣ የአቀናባሪው ነው ብለሽ ልታልፊው የምትችይው አይደለም፡፡ እጅግ በርካታ ችግሮች አሉበት፡፡ በዚህ የተነሳ የሙዚቃ ባለሙያዎችንም ህይወት አዳክሟል፡፡ ሙዚቃው እየተደጎመ ባለመሆኑ፣ ለምሳሌ ድሮ አንድ ብር ትገዢው የነበረው ሻማ አራት ብር ሲገባ፣ ሲዲ በድሮው ዋጋው እየተሸጠ እንኳን ጥበቡን አድንቆ የሚገዛ በመጥፋቱ የዘርፉ ባለሙያዎች የሚገባቸውን ገንዘብ እያገኙ አይደለም፡፡

የቤት ኪራይ የሚከፍሉት፣ የሚለብሱትና ቤተሰባቸውን የሚያስተዳድሩበት ገንዘብ እያጡ ባሉበት ሁኔታ፣ ነፃ ጥበብ መፍጠርና በፈጠራ የነጠሩ እንዲሆኑ መጠበቅ የማይታሰብ ነው፡፡ ይሄም ለኢንዱስትሪው ማደግ ማነቆ ከሆኑት አንዱ ነው ማለት ይቻላል? አንዱ ብቻ ሳይሆን ዋነኛውም ነው፡፡ ሙዚቃ አትራፊ እየሆነ ዘርፉ እያደገ ሲመጣ፣ ሙዚቀኛውም ለአዲስ ስራና ለፈጠራ ይነቃቃል፡፡ ወደ ዘርፉ የሚቀላቀሉ ባለሀብቶችም ይበዛሉ፡፡ አሁን ግን ደክመሽ ሰርተሽ በህገ-ወጥ መንገድ ሌሎች ሲጠቀሙበት ተስፋ ያስቆርጣል፡፡ በአሁኑ ሰዓት የፊልሙን ኢንዱስትሪ ተመልከቺ፤ አትራፊ ነው ስለሚባል ብዙ ባለሀብቶች እየተሳተፉበት ነው፡፡ ወደ ሙዚቃው ስትመጪ ግን ብዙ ውስብስብ ችግሮች ስላሉት፣ነባሮቹና በደንብ ይሰራሉ የሚባሉትም ከዘርፉ ወጥተዋል፡፡ አዲስ ሰው እንዳይገባ አትራፊ አይደለም፤ ይሄ ነው የእኛ አገር የሙዚቃ ጉዳይ፡፡ ታዲያ ይህ ሁሉ ችግር ባለበት አንተ እንዴት ደፍረህ ገባህ? አንደኛ ሙዚቃ ለእኔ ህይወቴ ነው! ሳትዘፍን ኑር ብትይኝ የማይሆን ነገር ነው፤ ምክንያቱም የምወደው ሙያ ነው፡፡ ከልጅነቴ ጀምሮ መሆን የምፈልገውን ነው የሆንኩት፡፡ እኔ ለምሳሌ የተለያዩ ስራዎች እሞክራለሁ፡- ሙዚቃው አለ፣ ጋዜጠኝነቱም አለ፤ የቴሌቪዥን ሾው አለኝ፡፡

አንዱ አንዱን እየደጎመ እጓዛለሁ፡፡ ነፍሴን ግን ለሙዚቃው ታደላለች፡፡ ሌላ ስራም ባልሰራ፣ የሚደጉመኝ ባይኖርም ከሙዚቃው እጅ ሰጥቼ አልወጣም፡፡ የነፍስ ጥሪሽ ከሆነ፣ የሙዚቃ ኢንዱስትሪው ደከመ ብለሽ ከዘርፉ አትወጪም፡፡ በቃ ሙዚቃ ልክፍት ነው፡፡ የሰው ዘፈን ይዘፍናሉ የምትያቸው እንኳን ከከበባቸው ችግር አኳያ ለአዲስ ፈጠራ ይቸገሩ ይሆናል እንጂ ከሙዚቃው አይወጡም፡፡ እንደነገርኩሽ በተለያዩ ፈታኝ ችግሮች ውስጥ አልፌ፣ከስድስት ዓመት በኋላ አልበሜን ዳር አድርሻለሁ፡፡ እዚህ እስክደርስ ድረስ ግን “ይሄ ይለቅ እንጂ ሁለተኛ አልበም የሚባል ልሰራ?” ስል ነው የቆየሁት፡፡ ያ ሁሉ አልፎ አልበሜን ስለቅ ግን፣ ቀጣዩን አልበም በምን መልኩ መስራት እንዳለብኝ ማሰብ ጀመርኩ፡፡ “መቼ ነው” በሚል ስያሜ ስለወጣው አዲስ አልበምህ ንገረኝ… አብዛኛው የአልበሙ ይዘት ፍቅር ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ፍቅር የሁሉም ነገር መሰረት ነው፡፡ እግዚአብሔር ፍቅር ነው፡፡ አንድነትን የሚያቀነቅን ዘፈንም አለ፡፡

ጉራጊኛ ዘፈኑን ብትወስጂ አንድ መሆንን፣ ህብረት መፍጠርን፣ በጋራ ማደግን የሚሰብክ ነው፡፡ በሰል ብሎ የተሰራውና የአልበሙ መጠሪያ የሆነው “መቼ ነው” የሚለውን የፍቅር ዘፈን ደግሞ ለእናቴ ነው የዘፈንኩት፤ ለእህቶቼም ጭምር፡፡ እህቶቼ ለእኔ ፊት ለፊት ገንዘብ መስጠት ባይችሉ እንኳን ችግር እንዳይገጥመኝ የሚያስፈልገኝን ነገር ከጓደኞቼ በመጠየቅ እየደጎሙኝ ነው ያደግሁት፡፡ እናቴም እኔን ብቻ ሳይሆን ቤተሰቡን እዚህ ለማድረስ ብዙ ደክማለች፡፡ ሴቶች ማለትም እናቶች፣ እህቶች፣ ሚስቶችና ፍቅረኞች በእኔ ውስጥ ትልቅ ቦታ አላቸው፡፡ ለምን መሰለሽ--- ሴት ልጅ ሄዳ ሄዳ እናትነት ጋ ነው የምትደርሰው፡፡ እናት ደግሞ ደሃም ትሁን ሀብታም፤ የተማረችም ትሁን ያልተማረች---ምንግዜም ፍቅሯ አይቀዘቅዝም፤ ማጣት አይለውጣትም፡፡ ሚስቶችን ተመልከቺ፤ ከራሳቸው በላይ ለባሎቻቸው ይኖራሉ፡፡ ለዚህ የተዘፈነ ነው፡፡ በሌላ በኩል ለወጣቶችና ለአድናቂዎቼ ሊያዝናናቸውና ፈታ ሊያደርጓቸው የሚችሉ ሞቅ ያሉ ዘፈኖችም አሉበት፡፡ በተጨማሪም ለየት የሚያደርገው ጉራጊኛ፣ ትግሪኛ፣ ጎንደርኛ እና የወሎንም ባህላዊ ዘፈኖች ማካተቴ ነው፡፡ በአገር ጉዳይ ላይም የዘፈንኩት አለ፡፡ በአጠቃላይ ሁሉም እንደየምርጫውና እንደየስሜቱ እንዲያዳምጠኝ በሚል 15 ጥሩ ጥሩ ዘፈኖችን በብፌ መልክ ደርድሬአለሁ፡፡ በግጥምና ዜማ ማን ተሳተፈ? ቅንብሩስ የእነማን ውጤት ነው? በዚህ አልበም ላይ የሚገርምሽ ነገር እኔ ራሴ አልበሙን ከጨረስኩኝ በኋላ ቁጭ ብዬ ስፅፍ ነው ሰባት አቀናባሪዎች መሳተፋቸውን ልብ ያልኩት፡፡ አብይ ኢርካ፣ ካሙዙ ካሳ፤ ትግርኛውን ያቀናበረው ሳምሶን ገ/አሊፍ ይባላል፡፡ እንዲሁም አሌክ ይለፍ፣ መኮንን ለማ እና ሚካኤል ሃይሉ አቀናብረውታል፡፡

ላይቭ ሙዚቃ የተጫወቱ፣ ፊቸሪንግ የገቡ፣ በድምፅ ያጀቡኝን ጨምሮ በአጠቃላይ ወደ 25 ሰዎች ተሳትፈውበታል፡፡ ወደ ግጥምና ዜማ ስንመጣ፣ መሰለ ጌታሁን፣ ጌትሽ ማሞ፣ ጃሉድ አወልና ሌሎችም አሉበት፡፡ “መቼ ነው” ሁለተኛ አልበምህ ነው፡፡ ከበፊቱ ስራህ ጋር እንዴት ታነጻጽረዋለህ? … ምን መሰለሽ---የመጀመሪያው ስራዬ በወቅቱ እንከን የለሽ ነበር ለእኔ፡፡ ያኔ የነበረኝን አቅምና የምችለውን ሁሉ አድርጌ ነው የሰራሁት፡፡ እንግዲህ የዛሬ 7 ዓመት ነው አልበሙ የወጣው፡፡ ለሁለተኛ ስራህ በጣም የዘገየህ አልመሰለህም? ዘግይቻለሁ፡፡ በነገርኩሽ የተለያዩ ችግሮች ምክንያት… ለኮንሰርት የተለያዩ አገራት መዞር አለ፡፡ ይሄ ሁሉ ተደምሮ ነው የዘገየሁት፡፡ የአሁኑን አልበሜን ስመለከተው ከበፊቱ የተለየ ስራ ይዤ መጥቻለሁ፡፡ ምክንያቱም በእድሜም በልምድም እየበሰልሽ ነው የምትሄጂው፡፡ የ25 ዓመት ወጣት ሆነሽ ስትዘፍኚና በ32 ዓመትሽ ስትዘፍኚ እኩል አይሆንም፡፡ ለምን? ከወጣትነት ወደ ጉልምስና ስትሄጂ፤ እየሰከንሽ፣ እያስተዋልሽና ኃላፊነት እየተሰማሽ ነው የምትመጪው፡፡ እንዳልኩሽ ያን ጊዜ ለእድሜዬና ለአቅሜ የሚመጥነውን ሰርቻለሁ፡፡ ከሰባት ዓመት በኋላ አይደለም ከአንድ ዓመት በኋላ የምሰራውም ልዩነት ማምጣት አለበት ብዬ አምናለሁ፤ ስለዚህ ጥሩና የበሰሉ ስራዎችን ይዤ መጥቻለሁ፡፡ የተገናኘነው ዛሬ አልበሙ ገበያ ላይ በዋለበት ቀን ነው (ማክሰኞ ከሰዓት ነበር) የዛሬ የገበያው ምን ይመስላል? በጣም ከጠበቅነው በላይ እየሸጥን ነው፡፡ በዚህም ደስተኞች ነን፡፡

ዛሬ እጅግ በጣም ጥሩ እንቅስቃሴ አይቻለሁ፡፡ አሳታሚው ማን ነው? የሚያከፋፍለውስ? እራሴ ነኝ ያሳተምኩት፤ የማከፋፈሉን ስራ “ፍሉት ኢንተርቴይመንት” እያከናወነው ይገኛል፡፡ ስፖንሰርን በተመለከተ ከፍተኛ እገዛ ያደረገልኝ ዳሽን ቢራ ነው፡ በዚህ አጋጣሚ በጣም ላመሰግናቸው እፈልጋለሁ፡፡ ምክንያቱም የሙዚቃ ኢንዱስትሪው በተዳከመበት በአሁኑ ወቅት ከምጠብቀው በላይ እንደውም አልበም በማሳተም ታሪክ ውስጥ ከፍተኛውን እገዛ አድርገውልኛል፡፡ ዳሽን ቢራ በቲቪ ሾው የበዓል ዝግጅቴ ላይ ተባባሪዎቼ ናቸው፡፡ ማሳተሚያው ምን ያህል ፈጀ? በተለያዩ ምክንያቶች የገንዘቡን መጠን መጥቀስ አልፈልግም፡፡ ብቻ ዳሽኖች ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርገውልኛል፡፡ በዚህ ምክንያት አልበሙን በምፈልገው ጥራትና ሁኔታ ለማሳተም ችያለሁ፡፡ ለማስተዋወቅም የገንዘብ እጥረት ገጥሞኝ አልሰስትም፤ ይሄ ሁሉ በእነርሱ ነው የሆነው፡፡ በኢቢኤስ በምታዘጋጀው “ጆሲ ኢን ዘ ሃውስ” ቲቪ ፕሮግራም ላይ በምታከናውናቸው የበጎ አድራጎት ስራዎች ከፍተኛ ተቀባይነት ማግኘትህ ይታወቃል፡፡ በተለይ ለድምፃዊ ማንአልሞሽ ዲቦ ልጆች ያደረግኸው ነገር የብዙዎችን ልብ ነክቷል፤ ሆኖም ከዚያን ጊዜ በኋላ ጆሲ ከመዝናኛ ፕሮግራሙ ይልቅ ወደ በጎ አድራጎቱ አዘንብሏል የሚሉ አስተያቶች ይሰነዘራሉ… እስቲ እኔ ደግሞ ጥያቄሽን በጥያቄ ልመልስ፡፡ እኔ እንግዲህ ከአንድ ዓመት በፊት በፋሲካ ነው ፕሮግራሙን የጀመርኩት፡፡ በዓመቱ ለማንአልሞሽ ልጆች ያንን ካደረግሁ በኋላ፣ የትኛው ፕሮግራም ነው ከመዝናኛነት ወጥቶ መደ በጎ አድራጎት ስራ የሄደው? ከማንአልሞሽ ዲቦ ልጆች በኋላ አንድም የበጎ አድራጎት ፕሮግራም አልሰራሁም! በቃ መልሱ ይሄ ነው፡፡ ምክንያቱም ባለፈው ፋሲካ ጀምሬ በዓመቱ የልጆቹን ሾው እስክሰራ ድረስ 52 ሳምንታት አሉ፡፡ በተለያዩ ችግሮች ሁለት ወይም ሶስት ሳምንታት ፕሮግራሙ ከመቋረጡ ውጭ 50 ያህሉ የመዝናኛ ፕሮግራሞች ናቸው፡፡ ይህን አይነት አስተያየት የሚሰጡ ሰዎች አሉ ብዬ አላምንም፤ ካሉም ግን ከሌሎች ሰዎች ሃሳብ በተቃራኒው ለመቆም የሚፈልጉና የሃሳብ ልዩነት ማንሳት የሚፈልጉ ናቸው፡፡ በእነዚያ 52 ሳምንታት ከተሰሩት ውስጥ በጣም ጥቂት ፕሮግራሞች በእርዳታ ላይ ሳይሆን ሰውን የማስታወስ ስራ ላይ ያተኮሩ ነበሩ፡፡ ከዚያ ውጭ ፕሮግራሙን የጀመርንበትን አንደኛ ዓመት ስናከብር፣ ከሜሪጆይ ጋር ነው ያሳለፍነው፡፡ እንግዲህ ለአዲስ ዓመት፣ ለገና፣ ለፋሲካ እና ለአንደኛ ዓመታችን ያካሄድናቸው ፕሮግራሞችን ጨምሮ አምስቱ ብቻ ናቸው የበጎ አድራጎት ሥራ የተሰራባቸው፡፡ ሌላው 50 ሳምንት የመዝናኛ ፕሮራሞች ናቸው የተሰሩት፡፡

ከፋሲካ በኋላ ሌላ ፕሮግራም አልሰራንም፤ ምክንያቱም አዲሱን ሲዝን ለመጀመር የተለያዩ ድርጅቱን የማሳደግ፣ የመገንባትና የማስፋፋት ሥራ ላይ ነው የተጠመድነው፡፡ ስለዚህ ያነሳሽው ጥያቄ ትክክል አይደለም!! እኔ ለቴሌቪዥን ፕሮፖዛል ሳቀርብ የመዝናኛ ፕሮግራም ብዬ ነው፡፡ ሌላ ልስራ ብትይም አይፈቀድልሽም፡፡ ነገር ግን የመዝናኛ ፕሮግራሙ እየተወደደና ተመልካቹ እየበዛ ሲሄድ፣ በዚህ አጋጣሚ ሰዎች የተቸገሩ ወገኖቻቸውን እንዲረዱ፣ የተረሱትን እንዲያስታውሱ ትምህርት ለመስጠት ታስቦ ነው እነዚያ አምስት ልዩ ፕሮግራሞች የተዘጋጁት፡፡ ሌሎች የበዓል የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችን ተመልከቺ፡- የሞላላቸው፣ የደላቸው ወይም በአንድ ነገር ላይ ታዋቂ የሆኑ ሰዎች ቤት ተዘጋጅቶ ሲዘፈን፣ ሲጨፈር ነው የምትመለከቺው፡፡ እኔ ጋ ስትመጪ ይሄንን ስራ ብሎ የመከረኝ ሰው የለም፤ የውስጤ ሃሳብ ነው የገፋፋኝ፡፡ እሺ እነዚህ ሰዎች ደከሙ፤ ለአገራቸው ብዙ ለፉ፤ መስዋዕትነት ከፈሉና ተረሱ፤ ብናስታውሳቸው ምንድነው ችግሩ? በጎ አድራጎት ቢሆንስ ምንድነው ክፋቱ? በቅን ልቦና ካሰብነው፣ የእርዳታ ስራ ቢመስልስ ምን ችግር አለው ነው የእኔ ጥያቄ? እንደውም ኖሮኝ መርዳት ብችል ደስታውን አልችለውም፡፡ የሚደርሱኝ አስተያየቶች “እባክህ የተረሱ ወገኖችን ፈልግና እኛም የአቅማችንን እናድርግ” የሚሉ ናቸው፡፡ አልበም ከወጣ በኋላ ኮንሰርት ማዘጋጀት የተለመደ ነው፡፡ ምን አስበሃል? እንግዲህ ቅድሚያ ትኩረት የሰጠነው የአልበሙ ጉዳይ ላይ ነው፡፡

አሁን አልበሙ ተለቋል፡፡ ወደ አምስትና ስድስት ያህል ዘፈኖች ክሊፕ ሰርተንላቸው፣ መስከረም ላይ ከበፊቶቹ ጋር ቀላቅለን ለተመልካች ለማድረስ እየተጋን እንገኛለን፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ የቴሌቪዥን ዝግጅቱን ከበፊቱ በተሻለ መልክ ለማቅረብ ከፍተኛ ዝግጀት እያደረግን ነው፡፡ አሁን ያሉን ስራዎች እነዚህ ናቸው፡፡ የኮንሰርቱን ሁኔታ ለጊዜው አላሰብነውም፤ ወደፊት እንደ አስፈላጊነቱ የሚወሰን ይሆናል፡፡ ባይሆን የአልበም ምርቃት በቅርቡ ይኖረናል፡፡ የመዝጊያ መልዕክት ወይም ምስጋና አለህ ? አልበሙ ላይ የተሳተፉትን ሁሉ በጣም አመሰግናለሁ፡፡ ዳሽን ቢራ ፋብሪካንም እጅግ በጣም አመሰግናለሁ፡፡ ቤተሰቦቼን፣ ወዳጆቼንና አድናቂዎቼንም እንዲሁ ከልብ አመሰግናለሁ፡፡ ከዚህ በተረፈ ሳልረሳው አንድ ቁም ነገር ልንገርሽ፡፡ የማንአልሞሽን ልጆች ፕሮግራም ለመስራት ለፋሲካ ወደ ደብረዘይት እየሄድን ነበር፡፡ ለዳሽን ቢራ የስፖንሰር ጥያቄ ካቀረብኩ ቆይቻለሁ፡፡ አልበሙንም ለፋሲካ ለማውጣት ነበር ያሰብኩት፡፡

የስፖንሰር ጥያቄው የብዙ ሰዎችን ውሳኔ የሚፈልግ ስለሆነ እየተነጋገሩበት ነበር ማለት ነው፡፡ እኔ ደግሞ ረስቼው ስራዬን እየሰራሁ ነበር፤ እናም የማናልሞሽን ልጆች ከቤት ወስጄ ደብረዘይት አድርሼያቸው አብረን በሚኒባስ ተመልሰን ቤታቸውን ላስረክባቸው ዱከም ስደርስ፣ ከዳሽን ቢራ ተደወለልኝ፡፡ ከጠየቅኳቸው በላይ በጣም ትልቅ የሚባል ብር ፈቀዱልኝ፤ በጣም ገረመኝ፡፡ በዚያን ሰዓት ምን አልኩኝ? “አንተ የሰውን ቤት ስትሰራ፣ እግዚአብሔር ያንተን ቤት ይሰራል” ብዬ አሰብኩኝ፡፡ በዚያው ቅፅበት ምን አሰብኩ? “እግዚአብሔር ለእኔ ብር ሰጥቶኛል፤ አልበሙ ተሸጦ ከሚገኘው ትርፍ 50 በመቶው ለማስታወቂያ፣ 50 በመቶውን ደግሞ ለእርዳታ ድርጅት እሰጣለሁ” ብዬ ቃል ገብቻለሁ፤ ቃሌንም እጠብቃለሁ፡፡ ለማን ነው የምሰጠው? የሚለውን ለመወሰን በእጄ ላይ ያሉ የተለያዩ ፕሮፖዛሎችን ማየት አለብኝ፡፡ እነሱን ገምግሜ ቅድሚያ ለሚሰጠው ድርጅት ግልፅነት በተመላበት መልኩ እሰጣለሁ፡፡ በተረፈ “መቼ ነው” የሚለውን ዘፈኔን ለፍቅር መስዋዕትነት ለሚከፍሉ ሚስቶች፣ እናቶች፣ እህቶችና ፍቅረኞች ጋብዣለሁ፡፡ ለመላው የኢትዮጵያ ህዝብ እንኳን ለአዲሱ ዓመት በሰላምና በጤና አደረሳችሁ በይልኝ፤ አመሰግናለሁ!!

Published in ጥበብ

ክሪስ ፕሩቲ ስለ ዳግማዊ አፄ ምኒልክ እና እቴጌ ጣይቱ የፃፈችውን መፅሀፍ፣ ውብሸት ስጦታው (ክፉንድላ) ወደ አማርኛ በመመለስ “ዳግማዊ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ” በሚል ርዕስ አሳትሞ ሰሞኑን ለገበያ አውሏል፡፡ መፅሀፉ ስለኢትዮጵያዊያን ስም አወጣጥ፣ የጣይቱ 5ኛ ባል ስለሆኑት የሸዋው ንጉስ አፄ ምኒልክ፣ ስለጣይቱ የእቴጌነት ማዕረግ፣ ከጣልያን ጋር ስለተደረጉት የአምባላጌ፣ የመቀሌና የዓድዋ ጦርነቶችና በርካታ ተያያዥ ታሪኮች ተካተውበታል፡፡ በ18 ምዕራፍ ተከፋፍሎ በ459 ገፅ የተመጠነው መፅሀፉ፤ በ80 ብር ለገበያ የቀረበ ሲሆን ባሳለፍነው ሳምንት ደራሲያን፣ ሃያሲያንና ጋዜጠኞች በተገኙበት በእቴጌ ጣይቱ ሆቴል ተመርቋል፡፡

በጋዜጠኛ ዳዊት ንጉሱ ረታ ተፅፎ የተዘጋጀው “በ97 እና ሌሎችም” መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ መፅሃፉ የደራሲው የመጀመሪያ ስራው ሲሆን በ97 ምርጫና በተለያዩ ማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩር ነው ተብሏል፡፡ በ172 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ39ብር ከ55 ሳንቲም ለአንባቢያን ቀርቧል፡፡

            የቴዎድሮስ አለማየሁ “ኤሽታኦል” የተሰኘ ፊልም ነገ በሁሉም ሲኒማ ቤቶች ተመርቆ ለእይታ እንደሚቀርብ ኦፕቲመም መልቲ ሚዲያ ገለፀ፡፡ የልብ አንጠልጣይነት ዘውግ ያለው ይሄው የፍቅር ፊልም፤ አንድ ጎበዝ ገጣሚ መድረክ ላይ ግጥሙን ሲያቀርብ የተመለከተች አንዲት ቆንጆ በፍቅር ስትወድቅለትና አጠገቧ የነበረውን እጮኛዋን ስታስገርም የሚያስቃኝ ነው ተብሏል፡፡ ፊልሙ በኦፕቲመም መልቲ ሚዲያ የተዘጋጀ ሲሆን በዋና ዳይሬክተርነት ቴዎድሮስ አለማየሁ ችሎታውን አሳይቶበታል ተብሏል፡፡ የ1፡40 ርዝማኔ ያለው “ኤሽታኦል” ፊልም ላይ አብርሃም አስቻለው በደራሲነትና በረዳት ዳይሬክተርነት የተሳተፈ ሲሆን ዳዊት አባተ፣ ሄለን በድሉ፣ አብርሃም አስቻለው፣ ፀጋዬ አበጋዝ፣ ፀጋዬ ዘርፉ፣ ዮናስ ካሳሁን እና ፍሬው አበበ እንደተወኑበት ለማወቅ ተችሏል፡፡

የቴዎድሮስ አለማየሁ “ኤሽታኦል” የተሰኘ ፊልም ነገ በሁሉም ሲኒማ ቤቶች ተመርቆ ለእይታ እንደሚቀርብ ኦፕቲመም መልቲ ሚዲያ ገለፀ፡፡ የልብ አንጠልጣይነት ዘውግ ያለው ይሄው የፍቅር ፊልም፤ አንድ ጎበዝ ገጣሚ መድረክ ላይ ግጥሙን ሲያቀርብ የተመለከተች አንዲት ቆንጆ በፍቅር ስትወድቅለትና አጠገቧ የነበረውን እጮኛዋን ስታስገርም የሚያስቃኝ ነው ተብሏል፡፡ ፊልሙ በኦፕቲመም መልቲ ሚዲያ የተዘጋጀ ሲሆን በዋና ዳይሬክተርነት ቴዎድሮስ አለማየሁ ችሎታውን አሳይቶበታል ተብሏል፡፡ የ1፡40 ርዝማኔ ያለው “ኤሽታኦል” ፊልም ላይ አብርሃም አስቻለው በደራሲነትና በረዳት ዳይሬክተርነት የተሳተፈ ሲሆን ዳዊት አባተ፣ ሄለን በድሉ፣ አብርሃም አስቻለው፣ ፀጋዬ አበጋዝ፣ ፀጋዬ ዘርፉ፣ ዮናስ ካሳሁን እና ፍሬው አበበ እንደተወኑበት ለማወቅ ተችሏል፡፡

Page 1 of 20