Administrator

Administrator

‹‹ለእንዲህ ዐይነት ሰው ለምን ይህ ክብር ይሰጣል በሚል ከጣልያን መንግሥት ጋራ ተነጋግረናል›› - አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ‹‹እስር ቤት የገቡትን ሰዎች ያለአግባብ ያንገላቱትን፣ ቶርች ያደረጉትን በግለሰብ ደረጃ በሕግ እንጠይቃለን›› - አቶ ይልቃል ጌትነት በአበባየሁ ገበያው እና ዓለማየሁ አንበሴ ከመሠረታዊ ዴሞክራሲያዊ መብቶች አንዱ የኾነው ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ መብት ‹‹ኢትዮጵያ ውስጥ ቅንጦት ነው›› በተባለበት ወቅት ላይ እንገኛለን፡፡ አባባሉ÷ ከተራ ዜጎች ሳይኾን አማራጭ የ[መንግሥታዊ] ሥልጣን/የኀይል ማእከል ከኾኑትና ለዴሞክራሲያዊነትና ሰብአዊ መብቶች መከበር እንቆማለን ከሚሉት የተቃውሞ ፖሊቲካ ፓርቲ አመራሮችና የሲቪክ ማኅበራት ክፍሎች አንደበት ሲደመጥ መስማት÷ የአፈናው የከፋ ገጽታ መልክ አውጥቶ አካል ገዝቶ እንድናየው ያደርጋል፡፡

አመራሮቹ÷ ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ መብት ጨርሶ መከልከሉ ከቶም ጥያቄ ሊኾንብን፣ ሊያነጋግረንና ሊያስገርመን አይገባም ሲሉን ግን የኹኔታውን ተስፋ አስቆራጭነት በጉልሕ ያረጋግጥልናል፡፡ አቶ ዐሥራት ኣብርሃም የአረና ለዴሞክራሲና ሉዓላዊነት ፓርቲ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊና የመድረክ የሥራ አስፈጻሚ አባል ናቸው፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ መብት ስለሚገኝበት ድቅድቅ ጨለማ አስመልክተው ሲናገሩ÷ ‹‹ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ መብት ማንም ሊከለክለው የማይችል ሕገ መንግሥታዊ መብት መኾኑን ጠንቅቀን እናውቃለን፡፡ ከ1997 ዓ.ም. ወዲህ ግን ይህ መብት በተግባር የተከለከለ ኾኖ እናገኘዋለን፡፡

በኛ በኩል ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ይቅርና አባሎቻችን በጽ/ቤት ደረጃ ከሚያካሂዱት ስብሰባ እንኳ ሲወጡ ጠብቀው እያሰሯቸው ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ሰላማዊ ሰልፍ ቅንጦት ነው የሚኾነው፤›› ይላሉ፡፡ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ሕገ መግሥታዊ መብት መኾኑን ጠንቅቀው ቢያውቁም ይህን መብት የመጠቀም ዕድል ማግኘት ግን አለመቻላቸውን አቶ ዐሥራት ኣብርሃም ይናገራሉ፡፡ መብቱ በሕግ እንጂ በተግባር የተፈቀደ አለመኾኑን ተገንዝቦ አርፎ ከመቀመጥ ውጭ መብቱን ለማስከበር ገፍተው የሄዱበት አጋጣሚ እንደሌለ የሚናገሩት አቶ ዐሥራት÷ ‹‹ሓላፊነት የሚወስድ ፓርቲና አመራር እስካለ ድረስ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ መብትን መጠቀም ያስፈልጋል፤›› ይላሉ፡፡ ‹‹ክልክላውን የሚያደርገው አካል ርምጃውን ወደ እስር ከፍ ቢያደርገው ሁሉንም አካል ማሰር ስለማይችል በሂደት ሕግን ወደ ማክበር ሊመጣ ይችል ነበር፤›› የሚሉት አቶ ዐሥራት÷ መብት ለማስከበር የሚደረግ ትግል የምር መኾን እንዳለበት ያምናሉ፡፡

ትግሉ ደግሞ የኢሕአዴግን ባሕርይ ጠንቅቆ ከመረዳት በሚቀየስ ጠንካራና ሰላማዊ የመታገያ ስልት በማስቀመጥ እስከ መጨረሻው መሄድ ነው፡፡ የኢሕአዴግን አረንጓዴ መብራት እየተጠበቁ ብቻ በመንቀሳቀስ በተግባር ክልከላ የተደረገበትን የሰላማዊ ሰልፍ መብት ማስከበር እንደማይቻል የፓርቲው አመራር ያስረዳሉ፡፡ በሚልዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያንን በግፍ ላስጨፈጨፈው ዓለም አቀፍ ወንጀለኛ ማርሻል ሩዶልፍ ግራዚያኒ መታሰቢያ በስሙ ሐውልትና መናፈሻ መሥራት÷ ‹‹የአባቶቻችንን መሥዋዕትነት የሚያራክስ ነው›› በማለት የተቃውሞ ድምፃቸውን ባሰሙ ዜጎች ላይ የደረሰውን እናውቃለን፡፡ የኢትዮጵያ ተቆርቋሪ የግል ተነሣሽነት ማኅበር፤ ሰማያዊ ፓርቲና ባለራእይ ወጣቶች ማኅበር በጋራ በመኾን በሕጋዊ መንገድ አሳውቀው ለማካሄድ ባቀዱት ሰላማዊ ሰልፍ ላይ የወጡ ዜጎች ታስረዋል፡፡ ‹‹ይህ የአፈናው ዐይነተኛ ገጽታ ነው፤›› ይላሉ አቶ ዐሥራት፡፡ ‹‹የሰላማዊ ሰልፉ ሐሳብ የአገር ጉዳይ እንጂ የፖሊቲካ አጀንዳ እንደሌለው ግልጽ ነው፡፡ ሕዝብን የጨፈጨፉ ሰዎች ፍርድ ማግኘት ሲገባቸው ይባስ ብሎ መታሰቢያ ሊቆምላቸው አይገባም የሚለው ጉዳይ በሕግም በሞራልም የሚያስጠይቅ በመኾኑ አጀንዳነቱ የመንግሥት መኾን ነበረበት፡፡

አሁን ያለው መንግሥት የኢትዮጵያ መንግሥት ነኝ ብሎ ሃገር እያስተዳደረ ነው፡፡ ኢትዮጵያን የሚመለከት አጀንዳ እንደ አጀንዳ መደገፍ ነበረበት እንጂ በዚህ ጉዳይ ሰልፍ መከልከሉ፣ ከልክሎም የወጡትን ሰዎች ማሰሩ የሚገርም ነገር ነው፡፡›› በአቶ ዐሥራት እምነት÷ ኢሕአዴግ በሰላማዊ መንገድ ለሃገሪቱ ዲሞክራሲያዊነት ይጠቅማል በሚል እሳቤ የሕዝብን ጥያቄ አይቀበልም፡፡ ሰልፍ የሚያስወጡ በርካታ ጉዳዮች ቢኖሩም በተለይ ከ1997 ዓ.ም ወዲህ ሰልፍ ለማድረግ የሚያስችል አበረታች ነገር የለም፡፡ ስለዚህም ፖሊቲካዊ በኾኑ ጉዳዮች ላይ ሰልፍ የማድረግ መብትን እስከ መጨረሻው አሟጦ ከመጠቀም አንጻር ፓርቲዎች ብዙ መሥራት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ‹‹መብቱ የሚፈቅድለትን ያህል ለመጠቀም ታግሎ ለመታሰር ዝግጁ የኾነ የፖለቲካ አመራርና አባል መኖር አለበት፤›› የሚሉት አቶ ዐሥራት÷ ‹‹ማንም የራሱን መብት ማስከበር ካልቻለ ሌላ አካል መጥቶ መብቴን ያስከብርልኛል ማለት አይችልም፤›› ይላሉ፡፡ አሁን ያለው የዜጎች መብት ፅልመታዊ የኾነው በአደባባይ በሚታየው ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ ችሎታ አንጻር ብቻ ሳይኾን፣ ‹‹ፍርድ ቤት ሄጄ መብቴን አስከብራለኹ ማለትም ተስፋ አስቆራጭ ነው፡፡ ፍርድ ቤት አቤቱታ የማቅረብ መብት አለኝ በሚል ለመከራከር ቢሞከር ማስረጃ የለውም ተብሎ አቤቱታው ውድቅ ይኾናል፤›› ይላሉ አቶ ዐሥራት፡፡

‹‹ፍርድ ቤትን ብቸኛ አማራጭ አድርጐ መጠቀም የሚቻለው ነፃና ገለልተኛ መኾኑ የታመነበት የፍርድ ተቋም ሲኖር ነው፡፡ በኛ አገር እንደዚህ ዐይነቱ የፍርድ ቤት ተቋም እንደሌለ ደግሞ ይታወቃል፡፡›› አቶ ዐሥራት በመደራጀት፣ ሐሳብን በነጻነት መግለጽና ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ መብቶች መረጋገጥ ተስፋ የቆረጡ ይመስላሉ፡፡ መብትን ለማስከበር ጠንካራ ተፎካካሪ ፓርቲና ለመታገል የቆረጠ አመራር፣ አባላትና ሕዝብ ያስፈልጋል ባይ ናቸው፡፡ አለበለዚያ በተቃዋሚው በኩል÷ በየጊዜው መታፈንን ከማስተጋባት የዘለለ ፋይዳ የሌለው መብት የማስከበር ሥራ ሊሠራ እንደማይችል፣ ገዢው ፓርቲም የራሱን መቀመጫ ለማደላደል ሌት ተቀን ከመትጋት ውጪ ለሕዝብ መብት ደንታ ያለው ፓርቲ ሊኾን እንደማይችል የፓርቲው አመራር አረጋግጠው ይናገራሉ፡፡

የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀ መንበር አቶ ይልቃል ጌትነት÷ ‹‹የታላቋን ሃገር ኢትዮጵያ ታሪክ እየዘነጋን፣ በቀድሞ አባቶቻችን ደም ላይ እንደቆምን እየረሳን፣ ብሔራዊ ስሜት ከልጆቻችን ከትውልዶችም እየጠፋ ውሎ አድሮ አንድ ያደረገን ክር ሁሉ እየላላ ገመናችንን ለጠላቶቻችን እያጋለጥን ነው፡፡ አልፎ ተርፎ ደግሞ የእኛ ገዳዮች ብሔራዊ ጀግና ተብለው ሐውልት እየተሠራላቸው እኛ ምን ያህል ቁልቁል እየሄድን መኾኑን የሚያመለክት ነበርና ይህን መቃወም፣ አባቶቻችንን ማሰብ ስለነበረብን ይህን ለማስታወስ በሕገ መንግሥቱ ሰላማዊ ሰልፍ ስለማድረግ የሰፈረውን ተጠቅመን ለሚመለከተው አካል አሳውቀን ነበር ሰልፉን የጠራነው፡፡›› ይላሉ፡፡ ‹‹የ30 ሺሕ ሰዎች ደም ሳይገድበው መብታችንን የሚገፍ አካል ካለ፤ ይግፈፉን፤ ለዚያ ግን እኛ የመጨረሻውን ዋጋ ለመክፈል ዝግጁ ነን፤›› የሚሉት አቶ ይልቃል ቀጣይ አካሄዶቻቸውን ያመለክታሉ÷ ‹‹እስሩም ኾነ የሰላማዊ ሰልፍ ክልከላው በጉልበት የተደረገ ነው፡፡ እኛ ግን እስር ቤት የገቡትን ሰዎች ያለአግባብ ያንገላቱትን. ቶርች ያደረጉትን በግለሰብ ደረጃ በሕግ እንጠይቃለን፡፡

›› ‹‹የግራዚያኒ ሐውልት መቆሙ፣ መናፈሻ መሠየሙ አግባብ አይደለም›› የሚሉት ደግሞ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የውጭ ግንኙነት መምሪያ መምህር ሰሎሞን ቶልቻ ናቸው፡፡ በጉዳዩ ላይ የግል አስተያየታቸውን የሰጡን መምህሩ፤ ‹‹ታሪኩን የሚያውቅና ኢትዮጵያዊነቱ የሚቆረቁረው እያንዳንዱ ዜጋ በዋዛ የሚያየው ጉዳይ አይደለም፡፡ በሃገር ደረጃ የየትኛውም እምነት ተከታይ ይኹን ኢትዮጵያዊ ሁሉ ትላንት አባቶቻችንን፣ በምን ዐይነት ኹኔታ እንደጨረሰ፣ በቁም እንደቀበረ፣ ባካፋ ከርጉዝ ሴት ሆድ ፅንስዋን እያወጣ በአደባባይ የንጹሐንን ደም ያፈሰሰበት ነው፡፡ በሃገር ደረጃ ሁሉም ረጋ ባለ መልክ መክረው አንድ ውሳኔ ማስተላለፍ ይጠበቅባቸዋል፡፡›› ይላሉ፡፡ ‹‹ትላንት ባሳለፍነው የብፁዓን አባቶቻችን÷ አቡነ ጴጥሮስ እና አቡነ ሚካኤል÷ ደምና ሕይወት አንደራደርም፡፡ እንዲህ ዐይነት ሰው ለጣልያን ሕዝብና መንግሥት ሞዴል የሚኾነው ከምን አኳያ ነው፡፡

መልእክቱስ ምንድን ነው? እንደምንስ ዛሬ ሊነሣ ቻለ? መንግሥትና ሃይማኖት የተለያዩ ናቸው ብንልም በልማት፣ በሰላምና በጸጥታ፣ የሰው ልጆች በፍቅር ተከባብረው እንዲኖሩ፣ በመልካም አስተዳደር ዙሪያ ቤተ ክርስቲያናችን ከመንግሥት ጋራ በአጋርነት ትሰራለች፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የአገሪቱን ታሪክ በአደራ ተቀብላ አቆይታለች፡፡ በዩኔስኮ ደረጃ የተመዘገቡ የሦስት ሺሕ ዘመን መንፈሳዊና ቁሳዊ ቅርሶች ባሏት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ነው ያሉት፡፡ ጉዳዩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ብቻ የሚወሰን ሳይኾን መንግሥትንም ይመለከተዋል፡፡ ሲቪክ ማኅበራት፣ አባት አርበኞች፣ ተመራማሪዎችም ይኹኑ የሃገር መልካም ገጽታ ግንባታ የሚቆረቁራቸው ሁሉ አብረው ሊሰለፉበት ይገባል - እንደ መ/ር ሰሎሞን ቶልቻ፡፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ጉዳዩን የሚለከቱት ለየት ባለ መንገድ ነው፡፡ የግራዚያኒን ሐውልት ለመትከል የተንቀሳቀሰው የኅብረተሰብ ክፍል/ግለሰቦች÷ በጣሊያን መንግሥት ደረጃ ሳይኾን ከጣልያን ማእከላዊ መንግሥት ፍላጎትና ዕውቅና ውጭ በጣሊያን አንድ ግዛት ውስጥ የራሱ አስተዳደር ባለው አንድ አካባቢ የሚገኝ ነው፡፡ ይህ እንቅስቃሴ እንደተሰማ ከጣልያን መንግሥት ጋራ በዲፕሎማሲ ቻናል ተነጋግረናል፡፡ የፋሺዝም ታሪክ ያጠላበት የኢትዮ - ጣልያን ግንኙነት ሳንካ ሊገጥመው ይችላል፤ ፋሽዝም ደግሞ የኢትዮጵያም ብቻ ሳይኾን የጣልያን ሕዝብ ጠላት ነው፤ ለእንዲህ ዐይነት ሰው ለምን ይህ ክብር ይሰጣል በሚል ከጣልያን መንግሥት ጋራ ተነጋግረናል፡፡

የጣልያን መንግሥት እንደሚለው÷ ይህን ነገር ለማሠራት የተንቀሳቀሰው የኅብረተሰብ ክፍል በማእከላዊው መንግሥት አይታወቅም፤ እንቅስቃሴው የማእከላዊ መንግሥት አቋም አይደለም የሚል ምላሽ ነው ያገኘነው፡፡ ስለዚህ የኢትዮጵያ መንግሥት ጉዳዩን በዝምታ አልተመለከተውም፡፡ በሁለት አገሮች መካከል እንዲህ ዐይነት ነገር ሲፈጠር ‹‹ሌጋሲዎን ዲፕሎማሲ›› የሚባል ነገር አለ፡፡ ዝም ብሎ አይነገርም፡፡ መጀመሪያ ውይይት ይደረጋል፡፡ ንግግርና መግባባት ይደረጋል፤ በሂደት ነው፡፡ ጉዳዩ የኢትጵያን ሕዝብ እንደሚያስቆጣ፣ የሁለትዮሽ ግንኙነቱንም እንደሚጎዳ በእኛ ኤምባሲ በኩል ለጣልያን መንግሥት ተገልጾልታል፡፡

አምባሳደር ዲና በመጨረሻም ‹‹ኅብረተሰቡ እንደ ኅብረተሰብ በተለያዩ መንገዶች የሚያደርጋቸው ሰላማዊ ሰልፎች፣ ፒቲሽኖችና ሌሎች የተቃውሞ ተጽዕኖዎች በመጨረሻ ወደምንፈልገው ውጤት ሊያመሩ ይችላሉ፤›› ካሉ በኋላ እንቅስቃሴውን እስከ መጨረሻው ድረስ ተከታትሎ የማስቆም ጥረቱ÷ የሁለቱን ሃገሮች የቆየ ጤናማ ግንኙነት በማይጎዳና ያለፈውን ጠባሳ በማይቀሰቅስ መልኩ እንደሚቀጥል አመልክተዋል፡፡ ከዲፕሎማሲያዊ ጥረቱ ውጭ በኅብረተሰቡ ደረጃ ተጋግሎ ስለቀጠለው የተቃውሞ እንቅስቃሴ የውጭ ጉዳይ ቃል አቀባዩ እንዲህ ይበሉ እንጂ ሕዝባዊውን ዲፕሎማሲ አስመልክቶ በተጨባጭ የታየው ግን ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ ሕገ መንግሥታዊ መብትን በተግባር የሚከለክል ርምጃ ነው፡፡ ስማቸው እንዳይገለጽ የጠየቁ የሕግ ባለሞያ እንዳሉት÷ ከምርጫ 97 ወዲህ የአንድ ዴሞክራሲያዊ አገር መለኪያዎች የኾኑት የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግና ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ መብት መጀመሪያ ተራ በተራ በወጡት ሕጎችና ዐዋጆች ገደብ ተጣለባቸው፡፡

አሁን በመጨረሻ÷ ሰላማዊ ሰልፍ የማካሄድ ሕገ መንግሥታዊ መብት ለገዢው ፓርቲ አጀንዳዎች ማስተጋቢያ ብቻ የተሰጠ እስከ መምሰል ደርሷል፡፡ ይህም በተቃውሞው ሰፈር ያሉት አካላት ‹‹የመተንፈስ መብት ተከለከልን›› እስከማለት ደርሰው ሲያሰሙት የነበረው ምሬት የተቀላቀለበት አቤቱታ መደምደሚያ ማረጋገጫ ኾኗል፡፡ የተከለከለው ሕገ መንግሥታዊ መብት - ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ዴሞክራዊ መብት - ለኢትዮጵያውያን ቅንጦት ነው መባሉ እውነት ሳይኾን አይቀርም፡፡

የኢትዮጵያ ክለቦች በአፍሪካ ደረጃ በሻምፒዮንስ ሊግ እና በኮንፌደሬሽን ካፕ በተሳትፎ እና በውጤታማነት ከፍተኛ ደረጃ ከያዙት የአህጉሪቱ ክለቦች ተርታ ለመግባት ብዙ መስራት እንደሚጠበቅባቸው መረጃዎች አመለከቱ፡፡ ዘንድሮ በሁለቱ አህጉራዊ ውድድሮች ተሳታፊ የሆኑት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ወደ የምድብ ድልድል ለመግባት ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ይህ ስኬት ለኢትዮጵያ ክለቦች የአፍሪካ ደረጃ መሻሻል አስተዋፅኦ እንደሚኖረው ይጠበቃል፡፡ በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ በመሳተፍ ላይ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ ነገ በአዲስ አበባ ስታድዬም በ2ኛ ዙር ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታውን ከማሊው ክለብ ዲጆሊባ ጋር ያደርጋል፡፡ በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ኮንፌዴሬሽን ካፕ የሚሳተፈው ደደቢት በበኩሉ በ2ኛ ዙር ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታውን ከሜዳው ውጭ በመጓዝ ከሱዳኑ ክለብ አልሃሊ ሼንዲ ጋር ይጋጠማል፡፡

የኢትዮጵያ ክለቦች በአፍሪካ ትልልቅ የክለብ ውድድሮች በነበራቸው የተሳትፎ ታሪክ ከማጣርያ ምእራፍ አልዘለለም፡፡ የኢትዮጵያ ክለቦች በአፍሪካ ያላቸውን ደረጃ ለማሻሻልና ያለባቸውን የፋይናንስ ችግርን ለመቅረፍ በአህጉራዊ የክለብ ውድድሮች የምድብ ድልድል መግባት ያግዛቸዋል፡፡ ይህ ስኬት ለአምስት አመታት በሚዘልቅ ውጤት ሲያጠናክሩ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን አሰራር መሰረት ነጥብ ያሰጣል፡፡ በአህጉራዊ ክለብ ውድድሮች በ3 ምእራፎች የሚደረጉ ማጣርያዎችን ለመቀነስም ወሳኝ ነው፡፡ በካፍ የውድድር አካሄድ መሰረት በሻምፒዮንስ ሊግ ሻምፒዮን መሆን አምስት ነጥብ፤ ሁለተኛ ደረጃ ማግኘት አራት ነጥብ፤ ግማሽ ፍፃሜ መግባት 3 ነጥብ፤ በምድብ ድልድል 3ኛ ደረጃ ማግኘት 2 ነጥብ እንዲሁም 4ኛ ሆኖ መጨረስ 1 ነጥብ ያስገኛል፡፡ በኮንፌደሬሽን ካፕ ደግሞ ሻምፒዮን መሆን አራት ነጥብ፤ ሁለተኛ ደረጃ ማግኘት ሶስት ነጥብ፤ ግማሽ ፍፃሜ መግባት 2 ነጥብ፤እንዲሁም በምድብ ድልድል 3ኛ እና 4ኛ ሆኖ መጨረስ 1 ነጥብ ያሰጣል፡፡ በሁለቱ ውድድሮች በአምስት የውድድር ዘመናት በሚገኝ ውጤት የሚገኘው ድምር ነጥብ በአፍሪካ እስከ 12ኛ ደረጃ ካስያዘ በየውድድሮቹ ከአንድ በላይ ክለቦችን ለማሳተፍ ያስችላል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ ከካፍ የሽልማት ገንዘብ ክለቦቹም ሆነ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ድርሻቸውን ያስገኝላቸዋል፡፡ በአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ ላይ ለምድብ ድልድል መድረስ ለክለብ ብቻ ሳይሆን ለሚወክለው ፌደሬሽንም የገንዘብ ጥቅም አለው፡፡ አንድ ክለብ በኮንፌደሬሽን ካፕ ሻምፒዮን ለመሆን ሲበቃ 625ሺ ዶላር ሲያገኝ የወከለው ፌደሬሽን 35ሺ ዶላር ይታሰብለታል፡፡ በሁለተኛነት ለክለቡ 432ሺ ዶላር ለፌደሬሽኑ 30ሺ ዶላር፤ በምድብ ሁለተኛ ሆኖ መጨረስ ለክለቡ 239ሺ ዶላር ለፌደሬሽኑ 25ሺ ዶላር፤ በምድብ በ3ኛ ደረጃ መጨረስ ለክለቡ 239ሺ ዶላር ለፌዴሬሽኑ 20ሺ ዶላር እንዲሁም በአራተኛ ደረጃ መጨረስ ለክለቡ 150ሺ ዶላር ለፌደሬሽኑ 15ሺ ዶላር ያስገኛል፡፡ በሌላ በኩል የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ከሽልማት ገንዘብ ለፌደሬሽኖች ድርሻ ባይኖርም ለየአገሩ ክለቦች ደረጃ ማደግና ለተጨዋቾቻቸው የፕሮፌሽናል እድል በመፍጠር ከፍተኛ ሚና አለው፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ሻምፒዮን በመሆን ዋንጫ የሚያነሳ ክለብ በሽልማት 1.5 ሚሊዮን ዶላር ከማግኘቱም በላይ በዓለም ክለቦች ዋንጫ አፍሪካን ወክሎ መሳተፍ እድል ይችላል፡፡ በካፍ ሻምፒዮንስ ሊግ በሁለተኛነት ደ 1 ሚሊዮን ዶላር፤ ለግማሽ ፍፃሜ በመድረስ 700ሺ ዶላር፤ በምድብ 3ኛ ደረጃን ይዞ መጨረስ 500ሺ ዶላር እንዲሁም በአራተኛ ደረጃ ማጠናቀቅ 400ሺ ዶላር ያስገኛል፡፡

በ2013 የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ደረጃ ላይ ለፓሪስ ሴንትዠርመን የሚጫወተው ዴቪድ ቤካም በ175 ሚሊዮን ፓውንድ የሃብት መጠን አንደኛ ሆነ፡፡ የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ በ115.5 ሚሊዮን ፓውንድ እንዲሁም የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ112 ሚሊዮን ፓውንድ ሃብታቸው ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ ብራዚላዊው ካካ በ66 ሚሊዮን ፓውንድ፤ ሮናልዲንሆ በ63 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የራሽያው አንዚ ማቻካላ ተጨዋች የሆነው ሳሙኤል ኤቶ በ52 ሚሊዮን ፓውንድ፤የማን ዩናይትዱ ዋይኔ ሩኒ በ50 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የፓሪስ ሴንትዠርመኑ ኢብራሞቪች በ47 ሚሊዮን ፓውንድ፤ ሪቫልዶ በ45.5 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የማን ዩናይትዱ ሪዮ ፈርዲናንድ በ42 ሚሊዮን ፓውንድ የሃብት መጠናቸው ከአራት እሰከ 10 ያለውን ደረጃ ወስደዋል፡፡ የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች እስከ 50ኛ ያላቸውን ደረጃን በመስራት ከሳምንት በፊት ይፋ ያደረገው ታዋቂው የእግር ኳስ ዘጋቢ ድረገፅ ጎል ነው፡፡

ጎል የዓለም የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ለመጀመርያ ጊዜ ለማዘጋጀት የቻለው ተጨዋቾች ያላቸውን በይፋ የሚታወቅ ሃብትና ንብረት፤ በተለያዩ ኩባንያዎች በሚያንቀሳቅሱት ገንዘብ፤ በደሞዝ ክፍያችው እና ቦነሳቸው እንዲሁም በማስታወቂያ እና በተለያዩ የንግድ ስራዎች የሚያገኟቸውን ገቢዎችን በማስላት ነው፡፡ በጎል ዶት ኮም የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ተብለው እስከ 50ኛ ደረጃ የተሰጣቸው በአጠቃላይ የሃብታቸው ድምር 1.7 ቢሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ በደረጃው ላይ ከሚገኙ ተጨዋቾች 22 በመቶ ያህሉ የእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሲሆን የተቀሩት ከ18 የተለያዩ አገራት የተውጣጡ ናቸው፡፡ ስምንት ፈረንሳዊያን፤ 6 ጣሊያናዊያን፤ 5 ስፔናዊያንና 5 ብራዚላውያን ገብተዋል፡፡ በደረጃው ሰንጠረዥ አራት ትውልደ አፍሪካዊ ተጨዋቾች አሉ፡፡

ባላቸው ሃብት እስከ 50ኛ ደረጃ ካገኙት ተጨዋቾች መካከል 37 ያህሉ እድሚያቸው ከ30 አመት በላይ ነው፡፡ ከ50ዎቹ ሃብታም የእግር ኳስ ተጨዋቾች የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ከ25 በላይ ተጨዋቾች አስመዝግቦ 50 በመቶ ድርሻ ይዟል፡፡ የስፔኑ ላሊጋ በ46 በመቶ፤ የጣሊያኑ ሴሪኤ በ42 በመቶ፤ የፈረንሳዩ ሊግ 1 በ24 በመቶ እንዲሁም የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ በ12 በመቶ ድርሻ ተወክለዋል፡፡ በደረጃው የገቡት ተጨዋቾች ከ10 በላይ ትልልቅ ዋንጫዎችን በአገር ውስጥ የሊግ ውድድርና በአህጉር ደረጃ ያገኙ ሲሆን 80 በመቶ ያህሉ በአማካይ እና አጥቂ መስመር የሚሰለፉ ናቸው፡፡ ከ50ዎቹ ሃብታም የእግር ኳስ ተጨዋቺች 26 በመቶው ለሪያል ማድሪድ፤22 በመቶ ለቼልሲ፤ 18 በመቶ ለኤሲ ሚላን፤ 16 በመቶ ለባርሴሎና እና ለማን ዩናይትድ እንዲሁም 14 በመቶ ያህሉ ለጁቬንትስ ክለብ ተጫውተዋል፡፡

58ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ወደ ሩብ ፍፃሜ ምእራፍ ሲሸጋገር የውድድሩ የሃይል ሚዛን እንግሊዝን ሸሽቶ ለስፔንና ጀርመን ክለቦች እያጋደለ መምጣቱ ተረጋገጠ፡፡ ዘንድሮ ለሩብ ፍፃሜ የበቁት ስምንት ክለቦች ከአምስት አገራት የተውጣጡ ሲሆኑ ፤ ሶስቱ የስፔን ክለቦች ሪያል ማድሪድ፣ ባርሴሎና እና ማላጋ፤ ሁለት የጀርመን ክለቦች ባየር ሙኒክና ቦርስያ ዶትመንድ እንዲሁም የጣሊያኑ ጁቬንትስ፤ የቱርኩ ጋላታሰራይ እና የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን ናቸው፡፡

ከ17 አመታት በኋላ የእንግሊዝ ክለቦች ሳይወከሉ ቀርተዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ባለፉት 13 አመታት በነበሩት የውድድር ዘመናት የጣሊያን ክለቦች በ2001፣ በ2002 እና በ2009 እኤአ፤ የጀርመን ክለቦች በ2003፣ በ2004 እና በ2008 እኤአ፤ የስፔን ክለቦች በ2005 እኤአ በሩብ ፍፃሜ ለመግባት አልሆነላቸውም ነበር፡፡ የአርሰናሉ አሰልጣኝ አርሴን ቬንገር የእንግሊዝ ክለቦች የበላይነት በስፔን ላሊጋ እና በጀርመን ቦንደስ ሊጋ ክለቦች እየተሸረሸረ መምጣቱን እንደሚያሳይ ሲናገሩ ፤ የሪያል ማድሪዱ ጆሴ ሞውሪንሆ በበኩላቸው የእንግሊዝ ክለቦች ከአውሮፓ እግር ኳስ ሃያልነት ርቀዋል ለማለት ጊዜው ገና ነው ብለዋል፡፡

ለዋንጫው ድል ሁለቱ የስፔን ክለቦች ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና ከፍተኛ ግምት ሲኖራቸው የጀርመኑ ባየር ሙኒክ ተፎካካሪ ነው፡፡ የቱርኩ ክለብ ጋላተሳራይ በቀድሞ ክለባቸው የሻምፒዮንስ ሊግ ድልን ያጣጣሙትን አንጋፋዎቹን ዲድዬር ድሮግባ እና ዌስሊ ስናይደርን በመያዝ በታሪኩ ለመጀመርያ ጊዜ ለሩብ ፍፃሜ ስለበቃ ስኬታ ተብሏል፡፡ የጀርመኑ ቦርስያ ዶርትመንድ በአስደናቂ የቡድን መንፈሱ፤ የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን በተጠናከረ አቅሙ እንዲሁም የጣሊያኑ ጁቬንትስ በጠንካራው የተከላካይ መስመሩ ለዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ ማራኪ ገፅታ እንዳላበሱ ተወስቶላቸዋል፡፡ የጣሊያኑ ጁቬንትስ ከ7 አመታት በኋላ፤የጀርመኑ ቦርስያ ዶርትመንድ ከ15 አመታት በኋላ እንዲሁም የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን ከ18 አመታት በኋላ ለሩብ ፍፃሜ መብቃታቸው ነው፡፡

ባለፉት ሶስት አመታት በሻምፒዮንስ ሊጉ ሲደበዝዝ የቆየው የእንግሊዝ ክለቦች ተፎካካሪነት ዘንድሮ በጥሎ ማለፍ ምእራፍ ማብቃቱ የፕሪሚዬር ሊጉ የበላይነት ሙሉ ለሙሉ ማክተሙን አሳይቷል፡፡ እንግሊዝን በመወከል ተሳታፊ ከነበሩት 4 ክለቦች መካከል ማን ሲቲ እና የአምናው የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ቼልሲ የተሰናበቱት ከምድብ ማጣርያው ነበር፡፡ ማን ዩናይትድና አርሰናል ደግሞ ሩጫቸው በጥሎ ማለፍ ምእራፍ አብቅቷል፡፡ ዘ ጋርዲያን በሰራው አሃዛዊ ስሌት መሰረት በዘንድሮ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የእንግሊዝ ክለቦች አሸናፊነት በአራተኛ ደረጃ የሚመደብ ሆኗል፡፡ በአሸናፊነት ግንባር ቀደም የሆነው የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ54 በመቶ ውጤታማነቱ ነው፡፡ የስፔኑ ላሊጋ በ53 በመቶ ፤የጣሊያን ሴሪኤ በ50 በመቶ ውጤታማነታቸው ተለክቷል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ውጤታማነት በ39 በመቶ ዝቅተኛው ነው፡፡ የጋርድያን ዘገባ እንዳመለከተው የእንግሊዝ ክለቦች ዘንድሮ ባሳዩት ድክመት በሻምፒዮንስ ሊግ የተሳትፎ ኮታ ላይ ቅናሽ እንዲመጣባቸው ሊያደርግ ይችላል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ለሊጎች በሚሰጥ የተሳትፎ ኮታ ወቅታዊ ደረጃ የስፔኑ ላሊጋ በ85.882 ነጥብ የመጀመርያ ደረጃ ይዟል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ79.82 ሁለተኛ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ76.75 ሶስተኛ እንዲሁም የጣሊያን ሴሪኤ በ63.4 ነጥብ አራተኛ ላይ ናቸው፡፡ በውድድር ዘመኑ መጨረሻ በዚሁ የሻምፒዮንስ ሊግ የተሳትፎ ኮታ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ወደ 3ኛ ደረጃ መውረዱ አይቀርም፡፡ ስለሆነም ለእንግሊዝ ክለቦች ለሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ቀጥታ ተሳትፎ የነበረው የአራት ክለቦች ኮታ ወደ ሶስት ይወርዳል ተብሏል፡፡ ዴይሊ ቴሌግራፍ በሰራው ዘገባ ደግሞ የእንግሊዝ ክለቦች ከሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፍ በመሰናበታቸው ለሩብ ፍፃሜ ፤ለግማሽ ፍፃሜ እና ለዋንጫ ጨዋታ በመድረስ በነፍስ ወከፍ እስከ 35 ሚሊዮን ፓውንድ የገቢ ድርሻም አጥተዋል፡፡

ከሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፍ የተሰናበተው ማን ዩናይትድ በተሳትፎው እስከ 34 ሚሊዮን ፓውንድ ሲያገኝ በተመሳሳይ ምእራፍ የቀረው አርሰናል እስከ 29.7 ሚሊዮን ፓውንድ ይኖረዋል፡፡ በምድብ ማጣርያው የተሰናበቱት የአምናው ሻምፒዮን ቼልሲ እስከ 29.4 ሚሊዮን ፓውንድ እንዲሁም ማን ሲቲ 27.8 ሚሊዮን ፓውንድ ገቢ እንደሚኖራቸውም የዴይሊ ቴሌግራፍ ስሌት አመልክቷል፡፡

በኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ስፖንሰርነት የአውሮፓ 24 ምርጥ ክለቦችን የሚያሳትፍ ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ስለመታቀዱ በለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የቀረበ ልዩ ዘገባ እውነታ አልተረጋገጠም፡፡ ኳታር በ2022 እኤአ ላይ በመካከለኛው ምስራቅ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲካሄድ የተፈቀደውን 22ኛው የዓለም ዋንጫ የምታዘጋጀው ናት፡፡ በሃሳቡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እንዳይቀየሙ ተሰግቷል፡፡ የለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ትልልቅ የአውሮፓ ክለቦች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› እንዲሳተፉ በማግባባት ላይ መሆናቸውን ሲዘግብ እስከ 175 ሚሊዮን ፓውንድ ለተሳትፏቸው ብቻ ለመክፈል ጥሪ አድርገጎላቸዋል ብሏል፡፡ ድሪም ፉትቦል ሊጉን በኳታር፤ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ፤ በሳውዲ አረቢያ እና በባህሬን በሚገኙ 6 ከተሞች በማዘዋወር በየሁለት ዓመቱ ለማካሄድ መታቀዱን የገለፀው ታይምስ አራቱ የእንግሊዝ ክለቦች ማን ዩናይትድ፤ ማን ሲቲ፤ አርሰናልና ቼልሲ እንዲሁም የስፔኖቹ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና በቀጥታ የተሳትፎ ግብዣ እንደቀረበላቸውም አውስቷል፡፡

በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› መጀመር ዙርያ ጥሪ ቀርቦላቸዋል የተባሉት እነዚህ ክለቦች በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጡት መግለጫ የለም፡፡ የኳታር እግር ኳስ ፌደሬሽን በኦፊሴላዊ ድረገፁ ስለ ድሪም ፉትቦል ሊጉ የሚወራውን ሲያስተባብል ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እስካሁን በጉዳዩ ላይ ይፋ መግለጫ ከማውጣት እንደተቆጠቡ ናቸው፡፡ የኳታር ባለሃብቶች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ከ9 አመታት በኋላ አገሪቱ ለምታዘጋጀው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ለማሟሟቅ ብለው ውድድሩን ያዘጋጁታል ያሉ ዘገባዎችም ወጥተዋል፡፡ ሌስ ካህሬስ ዴፉትቦል የተባለ የፈረንሳይ ሚዲያ በበኩሉ የለንደኑ ታይምስ ዘገባውን ከማሰራጨቱ አንድ ቀን ቀደም ብሎ የድሪም ፉትቦል ሊግ ጅማሮን በአዝናኝ ሃሳብነት ማቅረቡን ገልጿል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ በድሪም ፉትቦል ሊግ መጀመር ዙርያ የወጡ መረጃዎችን ለማጣራት እንደሚፈልግ የገለፁ አንዳንድ ዘገባዎች ከሻምፒዮንስ ሊግ እና በፊፋ ከሚዘጋጀው የዓለም ክለቦች ዋንጫ ጋር የሚመሳሰለው ውድድሩ እንዲካሄድ በምንም አይነት ፈቃድ እንደማይሰጥ አብራርተዋል፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ የገንዘብ ተፅእኖ እየጨመረ መጥቷል፡፡ በ2010 እኤአ ላይ ከኳታር የንጉሳውያን ቤተሰብ አንዱ የስፔኑን ክለብ ማላጋ በባለቤትነት ተያዘ፡፡ በ2011 እኤአ ላይ ሌሎች የንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት የፈረንሳዩን ፓሪስ ሴንትዠርመን በባለቤትነት ገዙ፡፡ ኳታር ፋውንዴሽን ደግሞ የታላቁ የስፔን ክለብ ባርሴሎና ማልያ በታሪክ የመጀመርያው ስፖንሰር መሆን እንደቻለ ይታወቃል፡፡

በኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ስፖንሰርነት የአውሮፓ 24 ምርጥ ክለቦችን የሚያሳትፍ ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ስለመታቀዱ በለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የቀረበ ልዩ ዘገባ እውነታ አልተረጋገጠም፡፡ ኳታር በ2022 እኤአ ላይ በመካከለኛው ምስራቅ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲካሄድ የተፈቀደውን 22ኛው የዓለም ዋንጫ የምታዘጋጀው ናት፡፡ በሃሳቡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እንዳይቀየሙ ተሰግቷል፡፡ የለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ትልልቅ የአውሮፓ ክለቦች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› እንዲሳተፉ በማግባባት ላይ መሆናቸውን ሲዘግብ እስከ 175 ሚሊዮን ፓውንድ ለተሳትፏቸው ብቻ ለመክፈል ጥሪ አድርገጎላቸዋል ብሏል፡፡ ድሪም ፉትቦል ሊጉን በኳታር፤ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ፤ በሳውዲ አረቢያ እና በባህሬን በሚገኙ 6 ከተሞች በማዘዋወር በየሁለት ዓመቱ ለማካሄድ መታቀዱን የገለፀው ታይምስ አራቱ የእንግሊዝ ክለቦች ማን ዩናይትድ፤ ማን ሲቲ፤ አርሰናልና ቼልሲ እንዲሁም የስፔኖቹ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና በቀጥታ የተሳትፎ ግብዣ እንደቀረበላቸውም አውስቷል፡፡

በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› መጀመር ዙርያ ጥሪ ቀርቦላቸዋል የተባሉት እነዚህ ክለቦች በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጡት መግለጫ የለም፡፡ የኳታር እግር ኳስ ፌደሬሽን በኦፊሴላዊ ድረገፁ ስለ ድሪም ፉትቦል ሊጉ የሚወራውን ሲያስተባብል ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እስካሁን በጉዳዩ ላይ ይፋ መግለጫ ከማውጣት እንደተቆጠቡ ናቸው፡፡ የኳታር ባለሃብቶች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ከ9 አመታት በኋላ አገሪቱ ለምታዘጋጀው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ለማሟሟቅ ብለው ውድድሩን ያዘጋጁታል ያሉ ዘገባዎችም ወጥተዋል፡፡ ሌስ ካህሬስ ዴፉትቦል የተባለ የፈረንሳይ ሚዲያ በበኩሉ የለንደኑ ታይምስ ዘገባውን ከማሰራጨቱ አንድ ቀን ቀደም ብሎ የድሪም ፉትቦል ሊግ ጅማሮን በአዝናኝ ሃሳብነት ማቅረቡን ገልጿል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ በድሪም ፉትቦል ሊግ መጀመር ዙርያ የወጡ መረጃዎችን ለማጣራት እንደሚፈልግ የገለፁ አንዳንድ ዘገባዎች ከሻምፒዮንስ ሊግ እና በፊፋ ከሚዘጋጀው የዓለም ክለቦች ዋንጫ ጋር የሚመሳሰለው ውድድሩ እንዲካሄድ በምንም አይነት ፈቃድ እንደማይሰጥ አብራርተዋል፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ የገንዘብ ተፅእኖ እየጨመረ መጥቷል፡፡ በ2010 እኤአ ላይ ከኳታር የንጉሳውያን ቤተሰብ አንዱ የስፔኑን ክለብ ማላጋ በባለቤትነት ተያዘ፡፡ በ2011 እኤአ ላይ ሌሎች የንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት የፈረንሳዩን ፓሪስ ሴንትዠርመን በባለቤትነት ገዙ፡፡ ኳታር ፋውንዴሽን ደግሞ የታላቁ የስፔን ክለብ ባርሴሎና ማልያ በታሪክ የመጀመርያው ስፖንሰር መሆን እንደቻለ ይታወቃል፡፡

ባለፈው ሳምንት በራሽያ ሰባት ሬስቶራንቶች ስላሏቸውና በቢሾፍቱ ---ሪዞርትን ስለከፈቱ ኢትዮጵያዊ ዶ/ር---- ሰፋ ያለ ቃለምልልስ አቅርበን ነበር፡፡ በቦታ ጥበት የተነሳ ኢንቨስተሩ ከራሽያ ማፍያዎች ጋር የነበራቸውን አስገራሚ ገጠመኞችና ውጣ ውረዶች ሳናቀርብ ቀርተናል፡፡ ዛሬ ይሄን ታሪካቸውን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡ ከኢንቨስተሩ ጋር ቃለምልልሱን ያደረገችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ናት፡፡ እስቲ ከራሽያ ማፍያዎች ጋር ስላሳለፉት ውጣ ውረድ ያጫውቱኝ----- ራሽያ ውስጥ ከ1990-2000 ዓ.ም ድረስ ትልቅ ቀውስ ነበር፡፡ ለአስር ዓመት አገሪቱን ማፍያዎች የተቆጣጠሩበት ዘመን ነበር፡፡ ብዙዎቹ ከሶሻሊዝም መፈረካከስ በኋላ ሃያ ዓመትና ከዛ በላይ ወህኒቤት ታስረው የተለቀቁ ናቸው፡፡ ፓፓ ወይም ‹‹የማፍያ አባት›› በመባል የሚታወቁ ሲሆኑ ሁሉም በሥራቸው ሁለት መቶና ሶስት መቶ ሰዎች ያደራጃሉ፡፡ ከተማውን በሙሉ እነዚህ ሰዎች ተከፋፍለውት ነበር፡፡

በየሰፈሩ አንድ አንድ የሰፈር አለቃ ይኖራል፡፡ በአንደኛው ፓፓ ግዛት ሌላው ጣልቃ በመግባት ለመበጥበጥ ቢሞክር የሰፈር አለቆች አደብ ያስገዙታል፡፡ ማንኛውም በቢዝነስ ውስጥ የተሰማራ ሰው ለእነሱ በየወሩ የተጣለበትን ክፍያ (ደሞዝ) ይከፍላል፡፡ ማነው ክፍያውን የሚወስነው? ሚር X የተባለ የማፍያው ቡድን አለቃ (ፓፓ ይሉታል) የንግድ ቦታሽ ድረስ ይመጣና ‹‹ከማን ጋር ነው የምትሰሪው?›› ብሎ ይጠይቅሻል፡፡ (ከየትኛው የማፍያ ቡድን ጋር ማለቱ ነው) ስሙን መናገር አለብሽ፡፡

ፓፓ ከሌለሽ በየቀኑ ተመላልሶ የሚሸጠውን፣የሚወጣ የሚገባውን አይቶ፣ አጥንቶና ሰልሎ በወር 5ሺ ዶላር ወይም 10 ሺህ ዶላር ክፍያ ሊመድብብሽ ይችላል፡፡ በየወሩ የተመደበብሽን ገንዘብ ባትከፍይ ቤትሽ በቦንብ ሊፈነዳ ወይም በእሳት ሊቀጣጠል ይችላል፡፡ በጥይት ሊገሉሽም ይችላሉ፡፡ ማንም የሚደርስልሽ የለም፡፡ መንግስት የለም ማለት ነው? እንደሌለ ቁጠሪው፡፡ እነሱ ከመንግስትና ከፖሊስ ቁጥጥር ውጭ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ ነገሩ ሳይገባሽ ለፖሊስ ወይም ለመንግስት ብታመለክቺ ጥይት በጭንቅላትሽ ላይ ይለቁብሻል፡፡ አንዳንዴ ለምሳሌ--አንቺ ካዛንቺስ የምትሰሪ ከሆነ----የልደታው ፓፓ (ንጉስ) ይመጣና ‹‹ለእኔ ይሄን ያህል መክፈል አለብሽ›› ብሎ ይወስንብሻል፡፡ ያኔ የፓፓሽን ስም ትጠሪያለሽ--- ካመነሽ ይሄዳል፡፡ ካላመነ ‹‹ደውልልኝ በይው›› ብሎ ስልኩን ትቶ ይሄዳል፡፡ ተደዋውለው ‹‹የእኔ ነው›› ከተባባሉ ነገሩ በዚያው ያልቃል፡፡ በቃ አንቺ ጋ አይደርሱብሽም ማለት ነው ፤ ለአንደኛው ብቻ ትከፍያለሽ፡፡

በዚህ ዓይነት ቢዝነስ ማስፋፋት አስቸጋሪ አይሆንም? አዎ!! ቢዝነስሽ እየሰፋ ሲመጣ ቢዝነስ በከፈትሽበት ቦታ ሁሉ ችግር ይገጥምሻል ----እንደአዲስ ክፍያ መጠየቅሽ አይቀርም፡ ለፓፓሽ ታሳውቂና እነሱ ተነጋግረው ስምምነት ያደርጋሉ፡፡ ይኼ የአንቺ ጉዳይ አይደለም፡፡ “እኔ ግዛት ውስጥ የአንተ “ቢዝነስማን” መጥቶ ስለሚሠራ፣ለአንተ ከሚከፍልህ አስር ሺህ ዶላር ውስጥ ሁለት ሺ ዶላሩን ለእኔ ትከፍለኛለህ፣ የእኔ ግዛት ነው›› ተባብለው እነሱው ይስማማሉ፡፡ አንቺ ፓፓሽ የወሰነብሽን ብቻ ነው የምትከፍይው፡፡ ማፍያዎቹ በቢዝነሳችሁ የሚያግዟችሁ--- የሚሰሩላችሁ ነገር አለ? በሬስቶራንቱ ውስጥ ጉልቤ ወይም ዱርዬ መጥቶ ሂሳብ አልከፍልም ካለ ደውለን እንነግራቸዋለን፣ መጥተው አንገቱን አንቀው አስከፍለውት ይሄዳሉ፡፡ ሌላ ችግር እፈጥራለሁ የሚል ካለም አንዱ የማፍያ አባት ከሁለት መቶ እስከ ሶስት መቶ የሚደርሱ ወታደሮች ስላሉት ችግር የለም፡፡ መጥተው አፍንጫውን ሰብረውት ይዘውት ይሄዳሉ፡፡

የገባሻትን ቃል ከጠበቅሽ ለደህንነትሽ ስጋት የለብሽም፡፡ እኔ እና አንቺ ስንሰራ ለምሳሌ ‹‹ስጋ አቀርብልሃለሁ›› ብለሽ ከእኔ መቶ ሺህ ብር ብትወስጅና ብትክጂኝ “ለፓፓ” እንጂ ለመንግስት ወይም ለፖሊስ ሪፖርት አታደርጊም፡፡ ፓፓው ቤትሽ መጥቶ ‹‹ያደረግሽው ነገር ጥሩ አይደለም፤ የእኛን ልጅ ሃቅ አጥፍተሻል፤ ስለዚህ በሳምንት ጊዜ ውስጥ ሁለት መቶ ሺ ብር ታመጪያለሽ›› ተብሎ ይበየንብሻል፡፡ ቅጣት መሆኑ ነው? አዎ ቅጣት ነው፡፡ ‹‹ይሄን ባትፈፅሚ ልጅሽን አታገኚውም፤ ባልሽ ከስራ አይመጣም፤ አንቺም ላትኖሪ ትችያለሽ›› በማለት አስጠንቅቀውሽ ይሄዳሉ፡፡ ስለዚህ ከየትም ታመጫታለሽ፤ ክህደት የሚባል ነገር አይወዱም፡፡ ነገር ግን አንቺን ለማስጠቃት ሆን ብዬ “መቶ ሺ አበድሬው አልመለሰልኝም›› ብዬ ብዋሽና አጣርተው ቢደርሱበት በተመሳሳይ ቅጣቱ በእኔ ላይ ይጣላል፡፡

ህግ አስከባሪ ማፍያዎች ማለትም ይቻላላ ..? ህግ አስከባሪዎች ናቸው (ሳቅ) ለምሳሌ ለመንግስት መክፈል ያለብሽን ታክስ ካልከፈልሽ አይለቁሽም፡፡ የተከራየሽውን ቤት ኪራይ በወቅቱ መክፈልም አለብሽ፡፡ በቢዝነስ ሥራ ውስጥ ከመንግስት የሚጠበቅብኝን ሁሉ መፈፀም አለብኝ፡፡ ስንት የማፍያ አባቶች ነበርዎት፤ያሳለፉት ውጣ ውረድ ምን ይመስላል? ብዙ ውጣ ውረዶች ነበሩ፡፡ የአንድ ቀበሌ ማፍያ አለቃ ድንገት ይመጣና ‹‹የአንተን የማፍያ አለቃ አላውቅልህም፤ ለእኔ ትከፍለኛለህ፡፡ ለእኔ ካልከፈልከኝ በግንባርህ ጥይት ነው የምለቅብህ›› ብሎ ይሄዳል፡፡ ወይንም ደግሞ ‹‹ነገ ጠዋት መቶ ሺህ ብር ይዘህ እንድትመጣ፣ እዚህ ቦታ መጥቼ እወስዳለሁ›› ሊልሽ ይችላል፡፡ ይሄኔ ለፓፓሽ ደውለሽ ትነግሪዋለሽ፡፡ እሱም ወይ ችግሩን በቀላሉ ተነጋግሮ ይፈታዋል አሊያም ደግሞ “አውቃቸዋለሁ፤እነሱ ጭንቅላታቸውን ያማቸዋል፤ ከእነሱ ጋር ያለኝን ችግር እስክፈታ ከአካባቢው ዞር ብትይ ይሻላል›› ብለው ይመክሩሻል፡፡

ችግሩ እስኪፈታ መኖርያ ቤት መቀየር አለብሽ፡፡ ሶስት አራት ጊዜ እንዲህ ፈትነውኛል፡፡ አንድ ጊዜ ምን አጋጠመኝ መሰለሽ.. ‹‹ጋጊስታን›› የሚባሉት እቤቴ መጡና.. ጋጊስታን ምንድን ናቸው? ተባራሪ ማፍያዎች ናቸው፡፡ እኛ ጎንደር፣ ጎጃም፣ ወሎ፣ ባሌ..እንደምንለው በየክፍለአገሩ ይኖራሉ፡፡ ‹‹እኛ ክልል መጥተህ በመስራትህ ለእኛ መክፈል ይገባሃል›› ይሉኛል፡፡ ‹‹እኔ እኮ የእራሴ ሰው (ፓፓ) አለኝ--- ለምን አትነጋገሩም?›› አልኳቸው፡፡ ‹‹ያንተን ፓፓ አናውቅም! ትከፍላለህ ትከፍላለህ›› ብለው አፋጠጡኝ፡፡ ጉድ ፈላ! እንደነዚህ አይነት ማፍያዎች ከተለያየ ቦታ መጥተው ዘርፈው ነው የሚሄዱት፡፡ ተንቀሳቃሽ ናቸው፡፡ አንዴ ቦጭቀው ይሄዳሉ፡፡ ለፓፓዬ ደወልኩና ነገርኩት፡፡

‹‹አንተ ጋ መጡ?›› አለኝ፡፡ ፓፓዬ አውቋቸዋል፡፡ ‹‹አዎ›› አልኩት፡፡ ‹‹ሌላም የገደሉት ሰው ስላለ ችግሩን እስክፈታው ሌላ አካባቢ ሂድና ቤት ተከራይተህ ተቀመጥ›› አለኝ፡፡ ሶስት ወር ሌላ አካባቢ ሄጄ ተቀመጥኩ፡፡ እነሱ ሲፈላለጉ፣ ሲቀጣጠሩ፣ ሲነጋገሩ ቆዩ - ‹‹የእኛ ነው፤ የእናንተ አይደለም፡፡ እኛ ነን በፊት የምናውቀው…ከየት ነው ያገኛችሁት፤ እኔ ነኝ አባቱ፤ አይደለህም›› የሚለውን ከተነጋገሩ በኋላ አንድ ቀን መጡና ይዘውኝ ሄዱ፡፡ “ንግግራችን ላይ አንተ መገኘት አለብህ” ብለው ነው የወሰዱኝ፡፡ አንድ ትልቅ ሬስቶራንት ምድር ቤት ውስጥ ነበር ውይይታቸው የተካሄደው፡፡ እኔን መሃል አደረጉኝና በግራና በቀኝ ሃያ ሃያ ሆነው ተቀመጡ - ‹‹የእኔ ልጅ ነው፤ የእኔ ልጅ ነው›› ክርክር ያዙ፡፡ ‹‹እናንተ የእኔ አባት ልትሆኑ አትችሉም፡፡

የወለደኝ ለገሠ ደምሴ የሚባል አባት አለኝ›› አልኳቸው (ሳቅ) እነሱ ግን ‹‹እኔ ነኝ መጀመሪያ ያየሁት›› ማለታቸው ነው፡፡ ከዛ እኔን የሚጠይቁኝን ከጠየቁኝ በኋላ ‹‹ውጣ›› አሉኝ፡፡ ለእኔ ጠባቂ ሰጥተውኝ፤ታጅቤ መኪና ይዤ ስለነበር ተሰባሰቡና “ከእርሱ ፀጉር አንድ ፀጉር ብትወድቅ ነፍስ ይጠፋል፤እንዳትተኩሱ መኪናውን አስነስቶ ይሂድ” ብለው ተናገሩ፡፡ (ይሄ ሁሉ እንግዲህ በጠራራ ፀሐይ መንግስት ባለበት ነው የሚካሄደው) ጠቡ ወደ መታኮስ የሚያመራበት ጊዜ የለም…? ብዙ ጊዜ ማፍያዎች ሲጣሉ አካፋና መዶሻ መኪና ላይ ጭነው ወደ መቃብር ሥፍራ ነው የሚሄዱት፡፡ እዚያ ይተኳኮሳሉ፤ይገዳደላሉ፡፡ የተረፉት አካፋቸውን ከመኪና ላይ አውርደው የሞተውን ቀብረው ወደቤታቸው ይመለሳሉ፡፡ መቃብር ቦታ ከሄዱ ጠንከር ያለ ጠብ ተፈጥሯል ማለት ነው፡፡ እነዚህ ማፍያዎች ቤተሰብ፣ ልጆች--- ምናምን የላቸውም እንዴ? በህጋቸው መሠረት ማፍያ ሚስት የማግባት መብት የለውም፣ ንብረት ማፍራት አይችልም፤ ከእናት አባቱ ጋር መኖር አይችልም፡፡ ክልክል ነው፡፡ የውስጥ ህግና ደንብ አላቸው፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አዕዋፋት ተሰብስበው እያደኑ ስለሚይዟቸው ጠላቶቻቸው ይወያያሉ፤ አሉ፡፡ ዋና ሰብሳቢያቸው ንሥር ነው፡፡ ንሥር ያቀረበው ሃሳብ የሚከተለው ነበር፡- “እንደምታውቁት የምንወያየው የጠላቶቻችንን ፈሊጥ ተረድተን ራሳችንን ለማዳን ምን እናድርግ በሚለው ላይ ሲሆን ለዚህ አስፈፃሚ የሚሆነንን ተወካይ በመጨረሻ ለመምረጥ ነው፡፡ የምንመርጠው ተወካይ

1ኛ/ ባላንጣዎቻችን ጋ ሄዶ ማሳመን የሚችል

2ኛ/ለመወዳደርና ለመመረጥ አቅም ያለው

3ኛ/ከነሱ ጋር ተግባብቶ ውስጣቸውን ጥሩ አድርጐ ለማየትና ለኛ ሪፖርት ለማድረግ የሚችል

4ኛ/ በአደጋ ጊዜ ፈጥኖ ሊርቃቸውና ሊያመልጥ የሚችል መሆን ይኖርበታል፡፡

ሰብሳቢው ንሥር ባቀረበው ቅድመ - ሁኔታ ላይ ሁሉም ተስማሙ፡፡ በዚህም መሠረት የተለያዩ አዕዋፋት ለምርጫ ቀረቡና በከፍተኛ ድምጽ የተመረጠችው ቆቅ ሆነች፡፡ ቆቅም ባደረገችው ንግግር፤ “ወንድሞቼ እህቶቼ፤ አዕዋፋት ሆይ! እናንተን እወክል ዘንድ ስለመረጣችሁኝና ዕምነታችሁን ስለጣላችሁብኝ ከልብ የመነጨ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፡፡ እንደምታውቁት በአሁኑ ጊዜ መመረጥ ከፍተኛ ፈተና ያለበት ነው፡፡ ምክንያቱም፤ ሀ) ባላንጦቻችን ከመቼውም የላቀ አንድነት ያላቸው ሰዓት በመሆኑ፤ ለ) በውድድሩ እንድንሳተፍ ያደረጉን ተሳትፎ እንዲኖረንና ሌሎቹ ጫካ ነዋሪ እንስሳት ስለደግነታቸው እንዲያደንቋቸው ስለሆነ፤ ሐ) ወዳጅና ጠላታቸውን ለመለየት ቢያንስ ከእኛ አንዱ በመካከላቸው እንዲገኝ ብለው ስላሰቡ፤ ይመስለኛል። ሆኖም ካለመሳተፍ መሳተፍ የበለጠ ጥቅም ይኖረዋልና እናንተን መስዬ፤ እናንተን አክዬ እና እናንተን ሆኜ ለመቅረብ ዝግጁ ነኝ፡፡ ይህንንም ለማሳካት ሦስት ዘዴዎችን ለመጠቀም እሞክራለሁ፡፡

1ኛው ወቅታዊነት ነው፡፡ 2ኛው ከእነሱ የሰፋ አስተሳሰብ ይዞ፣ ቀድሞ መገኘት ነው፡፡ 3ኛው እነሱን አለመናቅና ሊበልጡኝ የሚችሉበት አንዳንድ ጉዳይ እንደሚኖር ማመን ነው፡፡ ሁሉም በቆቅ ሃሳብ ተስማሙና አጨበጨቡላት፡፡ በመጨረሻ እርግብ እንድትናገር እድል እንዲሰጣት ጠየቀች፡፡ ተፈቀደላት፡፡ እርግብም፤ “ወንድሞቼ፣ እህቶቼ አዕዋፋት ሆይ! ቆቅ በመመረጧ እንደማናችሁም በጣም ተደስቻለሁ፡፡ ሆኖም አንድ ቅር ያለኝ ነገር አለ፡፡ ይኸውም፤ ቆቅ፤ “ቆቅ” የሚለውን ስሟን ይዛ የትም አትደርስም የሚል ዕምነት ነው ያለኝ፡፡ ስለዚህ ስሟን ብትቀይር ጥሩ ነው እላለሁ፡፡ ማን እንበላት ካላችሁም እኔ “ዋ-ኔ” የሚል ስም ቢሰጣት መልካም ነው እላለሁ አለች፡፡” ሁሉም መስማማታቸውን በክንፋቸው በማጨብጨብ ገለፁ፡፡ እርግብም ቀጥላ “አሁን የሚያዋጣን ዛሬ ከባላንጦቻችን መወዳጀት ነው” አለች፡፡ “ለነገስ?” ብለው ጠየቋት፡፡ “ለነገማ የሆዳቸውን ስናውቅ እንወስናለን!” አለች፡፡

*** ከጥበብ ሁሉ የሚልቀው ወቅትን ማወቅ ነው፡፡ ወቅትን አለማወቅ አቅምን ካለማወቅ እኩል ነው፡፡ “እያንዳንዱ ድል አንድ አንድ ጠላት እንደሚወልድ አትርሳ” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ ስለዚህም አሸነፍኩ ብሎ ዘራፍ ማለት ከመሸነፍ አንድ የሚሆንበት ጊዜ አለ፡፡ ድልን በማጭበርበር የምንቀዳጅ ከሆነም ዕድሜ ልካችንን እንቅልፍ እንዳይወስደን ያደርገናል፡፡ ፖለቲካ ብዙው እጁ ሸፍጥ ነው፡፡ ሁኔታዎችን ለራስ እንደሚመች ለማድረግ ማናቸውንም ዘዴ መጠቀም ይጠይቃል፡፡ ደራሲና ፀሐፌ ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን በአንደኛው ቴያትሩ እንዳለው፤ “አብዮትኮ ኳስ ጨዋታ ነው፡፡ አቀበለ፣ ተቀበለ፣ ይዞ ሄደ - መታ - ፎሪ ወጣ፤ አብዮቱ ከሸፈ ይባላል፤ ወይም ቀጥሎ ደግሞ “ይዞ ሄደ! አብዶ ሰራ! መታ! - ጐል! አብዮቱ ግቡን መታ!! ይባላል፡፡

ይሄው ነው አብዮት ማለት - ኳስ ጨዋታ ነው፡፡ መቼ እንደምናቀብል፣ መቼ ወደፊት እንደምንሄድ፣ መቼ አብዶ (ምሣ) እንደምንሠራ ካላወቅን ፖለቲከኛ መሆን አንችልም፡፡ ይህንን ምንጊዜም መርሳት የለብንም፡፡ “የጐጃም ትውልድ በሙሉ ከአባይ እስከ አባይ” በሚለው መጽሐፉ፤ ደራሲ ግርማ ጌታኹን፣ እንዲህ ይላል … “ወለተ አልፋ አመተ አልፍን ወለደች፡፡ ከዚህ የሚአሳዝን ታሪክ አለበት፡፡ በአገር ላይ ያለ ወንድ ሁሉ በጦርነት አልቆ ወንድ ተወዶ ሳለ፤ ወለተ አልፋና ዓመተ አልፋ ዲማ ገበያ ሲሄዱ፣ ዝያ የሚባል ውሃ ሞልቶ አንድ ወንድ ጐዳነኛ ወስዶት ከዛፍ ላይ ሰቅሎት አዩ፡፡ “ሰው ነህ ግንድ” አሉት፡፡ እርሱ ግን የውርጭ ድደን ጥርሱን ገጥሞት መናገር ቸግሮት ነበርና ከዛፉ አውርደው ፀሐይ ቢአሞቁት፤ ዘመድ ላይ ከጃራ ሹም የመጣሁ ነበርሁ፡፡

ግን ውሃው አዋረደኝ ተፋኝ አለና ተናገረ፡፡ የዚህ ጊዜ እናትና ልጆች የኔ ባል ይሁን የኔ ባል ይሁን ተባባሉበት፡፡ ተያይዘው ከዲማ መነኮሳት ከነአባ ተጠምቀ መድኅንና ከነአባ ዮሐኒ ዘንድ ለፍርድ ሄዱ፡፡ እኒያም ሲፈርዱ አንች ባል አግብተሺ ቤት ሠርተሺ እርስዋን ወልደሻል፡፡ እርሷ ባል ሳታገባ ሳትወልድ ልታረጅ ነውና ለርስዋ ይሁን፡፡ አንች ብታገኝ አግቢ፤ ብታቂ መንኩሺና ተቀመጪ፣ ብለው ፈረዱ ይባላል፡፡” ወንድ ሁሉ ካገር የሚጠፋበት ዘመን አያድርስብን፡፡ እናትና ልጅ በአንድ ባል የሚጣሉበትን ጊዜ አይጣልብን! ድፍረትን ከሀፍረት ሳንነጥል የምናይበት ዐይን ይስጠን - በተለይ በምርጫ ወቅት፡፡ ዘራፍ ማለት፣ አለሁ አለሁ ማለት፣ ያለ እኔ ማን አለ ማለት፣ ካለፈው አለመማር፤ ከመርገምት ሁሉ የከፋ መርገምት ነው፡፡ ምንጊዜም ቢሆን፤ “የሚባለው ነብር ከጓዳ ሳይወጣ የሚበላው ፍየል ተክለፍልፎ መጣ” የሚለውን አገርኛ ግጥም አንርሣ!

የንባብ ባህልን ማበረታታት ዓላማው አድርጎ መጋቢት 7 ቀን 2002 ዓ.ም ፕሮግራሙን የጀመረው “ብራና” የሬዲዮ ፕሮግራም ሦስተኛ ዓመቱን ነገ በ8 ሰዓት በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ ሲያከብር፣የሙዚቃ ተመራማሪው አርቲስት ሠርፀ ፍሬስብሃት “ለንባብ ባህል መዳበር የመንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ሚና” በሚል ርእስ ጥናቱን ያቀርባል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት “የኢትዮጵያውያን የንባብ ልምድ በሀገር ውስጥና በባህር ማዶ” በሚል ርእስ አስተውሎቶቹን በቃለ ምልልስ መልክ እንደሚያቀርብ ይጠበቃል፡፡ በ “እናት ማስታወቂያ” እየተዘጋጀ በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 የሚቀርበው የሬዲዮ ዝግጅት ዘወትር እሁድ ከምሽቱ 2 ሰዓት እስከ 4 ሰዓት በሚተላለፈው እያንዳንዱ ዝግጅት ላይ ጥያቄ ለሚመልሱ 10 አድማጮች መፃሕፍት እየሸለመ መሆኑን አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡