Administrator

Administrator

በ2013 የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ደረጃ ላይ ለፓሪስ ሴንትዠርመን የሚጫወተው ዴቪድ ቤካም በ175 ሚሊዮን ፓውንድ የሃብት መጠን አንደኛ ሆነ፡፡ የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ በ115.5 ሚሊዮን ፓውንድ እንዲሁም የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ112 ሚሊዮን ፓውንድ ሃብታቸው ሁለተኛ እና ሶስተኛ ደረጃ ላይ ናቸው፡፡ ብራዚላዊው ካካ በ66 ሚሊዮን ፓውንድ፤ ሮናልዲንሆ በ63 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የራሽያው አንዚ ማቻካላ ተጨዋች የሆነው ሳሙኤል ኤቶ በ52 ሚሊዮን ፓውንድ፤የማን ዩናይትዱ ዋይኔ ሩኒ በ50 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የፓሪስ ሴንትዠርመኑ ኢብራሞቪች በ47 ሚሊዮን ፓውንድ፤ ሪቫልዶ በ45.5 ሚሊዮን ፓውንድ፤ የማን ዩናይትዱ ሪዮ ፈርዲናንድ በ42 ሚሊዮን ፓውንድ የሃብት መጠናቸው ከአራት እሰከ 10 ያለውን ደረጃ ወስደዋል፡፡ የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች እስከ 50ኛ ያላቸውን ደረጃን በመስራት ከሳምንት በፊት ይፋ ያደረገው ታዋቂው የእግር ኳስ ዘጋቢ ድረገፅ ጎል ነው፡፡

ጎል የዓለም የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ለመጀመርያ ጊዜ ለማዘጋጀት የቻለው ተጨዋቾች ያላቸውን በይፋ የሚታወቅ ሃብትና ንብረት፤ በተለያዩ ኩባንያዎች በሚያንቀሳቅሱት ገንዘብ፤ በደሞዝ ክፍያችው እና ቦነሳቸው እንዲሁም በማስታወቂያ እና በተለያዩ የንግድ ስራዎች የሚያገኟቸውን ገቢዎችን በማስላት ነው፡፡ በጎል ዶት ኮም የእግር ኳስ ሃብታም ተጨዋቾች ተብለው እስከ 50ኛ ደረጃ የተሰጣቸው በአጠቃላይ የሃብታቸው ድምር 1.7 ቢሊዮን ፓውንድ ነው፡፡ በደረጃው ላይ ከሚገኙ ተጨዋቾች 22 በመቶ ያህሉ የእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሲሆን የተቀሩት ከ18 የተለያዩ አገራት የተውጣጡ ናቸው፡፡ ስምንት ፈረንሳዊያን፤ 6 ጣሊያናዊያን፤ 5 ስፔናዊያንና 5 ብራዚላውያን ገብተዋል፡፡ በደረጃው ሰንጠረዥ አራት ትውልደ አፍሪካዊ ተጨዋቾች አሉ፡፡

ባላቸው ሃብት እስከ 50ኛ ደረጃ ካገኙት ተጨዋቾች መካከል 37 ያህሉ እድሚያቸው ከ30 አመት በላይ ነው፡፡ ከ50ዎቹ ሃብታም የእግር ኳስ ተጨዋቾች የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ከ25 በላይ ተጨዋቾች አስመዝግቦ 50 በመቶ ድርሻ ይዟል፡፡ የስፔኑ ላሊጋ በ46 በመቶ፤ የጣሊያኑ ሴሪኤ በ42 በመቶ፤ የፈረንሳዩ ሊግ 1 በ24 በመቶ እንዲሁም የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ በ12 በመቶ ድርሻ ተወክለዋል፡፡ በደረጃው የገቡት ተጨዋቾች ከ10 በላይ ትልልቅ ዋንጫዎችን በአገር ውስጥ የሊግ ውድድርና በአህጉር ደረጃ ያገኙ ሲሆን 80 በመቶ ያህሉ በአማካይ እና አጥቂ መስመር የሚሰለፉ ናቸው፡፡ ከ50ዎቹ ሃብታም የእግር ኳስ ተጨዋቺች 26 በመቶው ለሪያል ማድሪድ፤22 በመቶ ለቼልሲ፤ 18 በመቶ ለኤሲ ሚላን፤ 16 በመቶ ለባርሴሎና እና ለማን ዩናይትድ እንዲሁም 14 በመቶ ያህሉ ለጁቬንትስ ክለብ ተጫውተዋል፡፡

58ኛው የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ወደ ሩብ ፍፃሜ ምእራፍ ሲሸጋገር የውድድሩ የሃይል ሚዛን እንግሊዝን ሸሽቶ ለስፔንና ጀርመን ክለቦች እያጋደለ መምጣቱ ተረጋገጠ፡፡ ዘንድሮ ለሩብ ፍፃሜ የበቁት ስምንት ክለቦች ከአምስት አገራት የተውጣጡ ሲሆኑ ፤ ሶስቱ የስፔን ክለቦች ሪያል ማድሪድ፣ ባርሴሎና እና ማላጋ፤ ሁለት የጀርመን ክለቦች ባየር ሙኒክና ቦርስያ ዶትመንድ እንዲሁም የጣሊያኑ ጁቬንትስ፤ የቱርኩ ጋላታሰራይ እና የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን ናቸው፡፡

ከ17 አመታት በኋላ የእንግሊዝ ክለቦች ሳይወከሉ ቀርተዋል፡፡ በሻምፒዮንስ ሊጉ ባለፉት 13 አመታት በነበሩት የውድድር ዘመናት የጣሊያን ክለቦች በ2001፣ በ2002 እና በ2009 እኤአ፤ የጀርመን ክለቦች በ2003፣ በ2004 እና በ2008 እኤአ፤ የስፔን ክለቦች በ2005 እኤአ በሩብ ፍፃሜ ለመግባት አልሆነላቸውም ነበር፡፡ የአርሰናሉ አሰልጣኝ አርሴን ቬንገር የእንግሊዝ ክለቦች የበላይነት በስፔን ላሊጋ እና በጀርመን ቦንደስ ሊጋ ክለቦች እየተሸረሸረ መምጣቱን እንደሚያሳይ ሲናገሩ ፤ የሪያል ማድሪዱ ጆሴ ሞውሪንሆ በበኩላቸው የእንግሊዝ ክለቦች ከአውሮፓ እግር ኳስ ሃያልነት ርቀዋል ለማለት ጊዜው ገና ነው ብለዋል፡፡

ለዋንጫው ድል ሁለቱ የስፔን ክለቦች ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና ከፍተኛ ግምት ሲኖራቸው የጀርመኑ ባየር ሙኒክ ተፎካካሪ ነው፡፡ የቱርኩ ክለብ ጋላተሳራይ በቀድሞ ክለባቸው የሻምፒዮንስ ሊግ ድልን ያጣጣሙትን አንጋፋዎቹን ዲድዬር ድሮግባ እና ዌስሊ ስናይደርን በመያዝ በታሪኩ ለመጀመርያ ጊዜ ለሩብ ፍፃሜ ስለበቃ ስኬታ ተብሏል፡፡ የጀርመኑ ቦርስያ ዶርትመንድ በአስደናቂ የቡድን መንፈሱ፤ የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን በተጠናከረ አቅሙ እንዲሁም የጣሊያኑ ጁቬንትስ በጠንካራው የተከላካይ መስመሩ ለዘንድሮው ሻምፒዮንስ ሊግ ማራኪ ገፅታ እንዳላበሱ ተወስቶላቸዋል፡፡ የጣሊያኑ ጁቬንትስ ከ7 አመታት በኋላ፤የጀርመኑ ቦርስያ ዶርትመንድ ከ15 አመታት በኋላ እንዲሁም የፈረንሳዩ ፓሪስ ሴንትዠርመን ከ18 አመታት በኋላ ለሩብ ፍፃሜ መብቃታቸው ነው፡፡

ባለፉት ሶስት አመታት በሻምፒዮንስ ሊጉ ሲደበዝዝ የቆየው የእንግሊዝ ክለቦች ተፎካካሪነት ዘንድሮ በጥሎ ማለፍ ምእራፍ ማብቃቱ የፕሪሚዬር ሊጉ የበላይነት ሙሉ ለሙሉ ማክተሙን አሳይቷል፡፡ እንግሊዝን በመወከል ተሳታፊ ከነበሩት 4 ክለቦች መካከል ማን ሲቲ እና የአምናው የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ቼልሲ የተሰናበቱት ከምድብ ማጣርያው ነበር፡፡ ማን ዩናይትድና አርሰናል ደግሞ ሩጫቸው በጥሎ ማለፍ ምእራፍ አብቅቷል፡፡ ዘ ጋርዲያን በሰራው አሃዛዊ ስሌት መሰረት በዘንድሮ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የእንግሊዝ ክለቦች አሸናፊነት በአራተኛ ደረጃ የሚመደብ ሆኗል፡፡ በአሸናፊነት ግንባር ቀደም የሆነው የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ54 በመቶ ውጤታማነቱ ነው፡፡ የስፔኑ ላሊጋ በ53 በመቶ ፤የጣሊያን ሴሪኤ በ50 በመቶ ውጤታማነታቸው ተለክቷል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ውጤታማነት በ39 በመቶ ዝቅተኛው ነው፡፡ የጋርድያን ዘገባ እንዳመለከተው የእንግሊዝ ክለቦች ዘንድሮ ባሳዩት ድክመት በሻምፒዮንስ ሊግ የተሳትፎ ኮታ ላይ ቅናሽ እንዲመጣባቸው ሊያደርግ ይችላል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ለሊጎች በሚሰጥ የተሳትፎ ኮታ ወቅታዊ ደረጃ የስፔኑ ላሊጋ በ85.882 ነጥብ የመጀመርያ ደረጃ ይዟል፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ79.82 ሁለተኛ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ76.75 ሶስተኛ እንዲሁም የጣሊያን ሴሪኤ በ63.4 ነጥብ አራተኛ ላይ ናቸው፡፡ በውድድር ዘመኑ መጨረሻ በዚሁ የሻምፒዮንስ ሊግ የተሳትፎ ኮታ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ወደ 3ኛ ደረጃ መውረዱ አይቀርም፡፡ ስለሆነም ለእንግሊዝ ክለቦች ለሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ቀጥታ ተሳትፎ የነበረው የአራት ክለቦች ኮታ ወደ ሶስት ይወርዳል ተብሏል፡፡ ዴይሊ ቴሌግራፍ በሰራው ዘገባ ደግሞ የእንግሊዝ ክለቦች ከሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፍ በመሰናበታቸው ለሩብ ፍፃሜ ፤ለግማሽ ፍፃሜ እና ለዋንጫ ጨዋታ በመድረስ በነፍስ ወከፍ እስከ 35 ሚሊዮን ፓውንድ የገቢ ድርሻም አጥተዋል፡፡

ከሻምፒዮንስ ሊጉ ጥሎ ማለፍ የተሰናበተው ማን ዩናይትድ በተሳትፎው እስከ 34 ሚሊዮን ፓውንድ ሲያገኝ በተመሳሳይ ምእራፍ የቀረው አርሰናል እስከ 29.7 ሚሊዮን ፓውንድ ይኖረዋል፡፡ በምድብ ማጣርያው የተሰናበቱት የአምናው ሻምፒዮን ቼልሲ እስከ 29.4 ሚሊዮን ፓውንድ እንዲሁም ማን ሲቲ 27.8 ሚሊዮን ፓውንድ ገቢ እንደሚኖራቸውም የዴይሊ ቴሌግራፍ ስሌት አመልክቷል፡፡

በኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ስፖንሰርነት የአውሮፓ 24 ምርጥ ክለቦችን የሚያሳትፍ ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ስለመታቀዱ በለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የቀረበ ልዩ ዘገባ እውነታ አልተረጋገጠም፡፡ ኳታር በ2022 እኤአ ላይ በመካከለኛው ምስራቅ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲካሄድ የተፈቀደውን 22ኛው የዓለም ዋንጫ የምታዘጋጀው ናት፡፡ በሃሳቡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እንዳይቀየሙ ተሰግቷል፡፡ የለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ትልልቅ የአውሮፓ ክለቦች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› እንዲሳተፉ በማግባባት ላይ መሆናቸውን ሲዘግብ እስከ 175 ሚሊዮን ፓውንድ ለተሳትፏቸው ብቻ ለመክፈል ጥሪ አድርገጎላቸዋል ብሏል፡፡ ድሪም ፉትቦል ሊጉን በኳታር፤ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ፤ በሳውዲ አረቢያ እና በባህሬን በሚገኙ 6 ከተሞች በማዘዋወር በየሁለት ዓመቱ ለማካሄድ መታቀዱን የገለፀው ታይምስ አራቱ የእንግሊዝ ክለቦች ማን ዩናይትድ፤ ማን ሲቲ፤ አርሰናልና ቼልሲ እንዲሁም የስፔኖቹ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና በቀጥታ የተሳትፎ ግብዣ እንደቀረበላቸውም አውስቷል፡፡

በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› መጀመር ዙርያ ጥሪ ቀርቦላቸዋል የተባሉት እነዚህ ክለቦች በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጡት መግለጫ የለም፡፡ የኳታር እግር ኳስ ፌደሬሽን በኦፊሴላዊ ድረገፁ ስለ ድሪም ፉትቦል ሊጉ የሚወራውን ሲያስተባብል ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እስካሁን በጉዳዩ ላይ ይፋ መግለጫ ከማውጣት እንደተቆጠቡ ናቸው፡፡ የኳታር ባለሃብቶች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ከ9 አመታት በኋላ አገሪቱ ለምታዘጋጀው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ለማሟሟቅ ብለው ውድድሩን ያዘጋጁታል ያሉ ዘገባዎችም ወጥተዋል፡፡ ሌስ ካህሬስ ዴፉትቦል የተባለ የፈረንሳይ ሚዲያ በበኩሉ የለንደኑ ታይምስ ዘገባውን ከማሰራጨቱ አንድ ቀን ቀደም ብሎ የድሪም ፉትቦል ሊግ ጅማሮን በአዝናኝ ሃሳብነት ማቅረቡን ገልጿል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ በድሪም ፉትቦል ሊግ መጀመር ዙርያ የወጡ መረጃዎችን ለማጣራት እንደሚፈልግ የገለፁ አንዳንድ ዘገባዎች ከሻምፒዮንስ ሊግ እና በፊፋ ከሚዘጋጀው የዓለም ክለቦች ዋንጫ ጋር የሚመሳሰለው ውድድሩ እንዲካሄድ በምንም አይነት ፈቃድ እንደማይሰጥ አብራርተዋል፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ የገንዘብ ተፅእኖ እየጨመረ መጥቷል፡፡ በ2010 እኤአ ላይ ከኳታር የንጉሳውያን ቤተሰብ አንዱ የስፔኑን ክለብ ማላጋ በባለቤትነት ተያዘ፡፡ በ2011 እኤአ ላይ ሌሎች የንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት የፈረንሳዩን ፓሪስ ሴንትዠርመን በባለቤትነት ገዙ፡፡ ኳታር ፋውንዴሽን ደግሞ የታላቁ የስፔን ክለብ ባርሴሎና ማልያ በታሪክ የመጀመርያው ስፖንሰር መሆን እንደቻለ ይታወቃል፡፡

በኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ስፖንሰርነት የአውሮፓ 24 ምርጥ ክለቦችን የሚያሳትፍ ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ስለመታቀዱ በለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የቀረበ ልዩ ዘገባ እውነታ አልተረጋገጠም፡፡ ኳታር በ2022 እኤአ ላይ በመካከለኛው ምስራቅ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲካሄድ የተፈቀደውን 22ኛው የዓለም ዋንጫ የምታዘጋጀው ናት፡፡ በሃሳቡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እንዳይቀየሙ ተሰግቷል፡፡ የለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ትልልቅ የአውሮፓ ክለቦች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› እንዲሳተፉ በማግባባት ላይ መሆናቸውን ሲዘግብ እስከ 175 ሚሊዮን ፓውንድ ለተሳትፏቸው ብቻ ለመክፈል ጥሪ አድርገጎላቸዋል ብሏል፡፡ ድሪም ፉትቦል ሊጉን በኳታር፤ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ፤ በሳውዲ አረቢያ እና በባህሬን በሚገኙ 6 ከተሞች በማዘዋወር በየሁለት ዓመቱ ለማካሄድ መታቀዱን የገለፀው ታይምስ አራቱ የእንግሊዝ ክለቦች ማን ዩናይትድ፤ ማን ሲቲ፤ አርሰናልና ቼልሲ እንዲሁም የስፔኖቹ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና በቀጥታ የተሳትፎ ግብዣ እንደቀረበላቸውም አውስቷል፡፡

በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› መጀመር ዙርያ ጥሪ ቀርቦላቸዋል የተባሉት እነዚህ ክለቦች በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጡት መግለጫ የለም፡፡ የኳታር እግር ኳስ ፌደሬሽን በኦፊሴላዊ ድረገፁ ስለ ድሪም ፉትቦል ሊጉ የሚወራውን ሲያስተባብል ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እስካሁን በጉዳዩ ላይ ይፋ መግለጫ ከማውጣት እንደተቆጠቡ ናቸው፡፡ የኳታር ባለሃብቶች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ከ9 አመታት በኋላ አገሪቱ ለምታዘጋጀው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ለማሟሟቅ ብለው ውድድሩን ያዘጋጁታል ያሉ ዘገባዎችም ወጥተዋል፡፡ ሌስ ካህሬስ ዴፉትቦል የተባለ የፈረንሳይ ሚዲያ በበኩሉ የለንደኑ ታይምስ ዘገባውን ከማሰራጨቱ አንድ ቀን ቀደም ብሎ የድሪም ፉትቦል ሊግ ጅማሮን በአዝናኝ ሃሳብነት ማቅረቡን ገልጿል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ በድሪም ፉትቦል ሊግ መጀመር ዙርያ የወጡ መረጃዎችን ለማጣራት እንደሚፈልግ የገለፁ አንዳንድ ዘገባዎች ከሻምፒዮንስ ሊግ እና በፊፋ ከሚዘጋጀው የዓለም ክለቦች ዋንጫ ጋር የሚመሳሰለው ውድድሩ እንዲካሄድ በምንም አይነት ፈቃድ እንደማይሰጥ አብራርተዋል፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ የገንዘብ ተፅእኖ እየጨመረ መጥቷል፡፡ በ2010 እኤአ ላይ ከኳታር የንጉሳውያን ቤተሰብ አንዱ የስፔኑን ክለብ ማላጋ በባለቤትነት ተያዘ፡፡ በ2011 እኤአ ላይ ሌሎች የንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት የፈረንሳዩን ፓሪስ ሴንትዠርመን በባለቤትነት ገዙ፡፡ ኳታር ፋውንዴሽን ደግሞ የታላቁ የስፔን ክለብ ባርሴሎና ማልያ በታሪክ የመጀመርያው ስፖንሰር መሆን እንደቻለ ይታወቃል፡፡

ባለፈው ሳምንት በራሽያ ሰባት ሬስቶራንቶች ስላሏቸውና በቢሾፍቱ ---ሪዞርትን ስለከፈቱ ኢትዮጵያዊ ዶ/ር---- ሰፋ ያለ ቃለምልልስ አቅርበን ነበር፡፡ በቦታ ጥበት የተነሳ ኢንቨስተሩ ከራሽያ ማፍያዎች ጋር የነበራቸውን አስገራሚ ገጠመኞችና ውጣ ውረዶች ሳናቀርብ ቀርተናል፡፡ ዛሬ ይሄን ታሪካቸውን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡ ከኢንቨስተሩ ጋር ቃለምልልሱን ያደረገችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ናት፡፡ እስቲ ከራሽያ ማፍያዎች ጋር ስላሳለፉት ውጣ ውረድ ያጫውቱኝ----- ራሽያ ውስጥ ከ1990-2000 ዓ.ም ድረስ ትልቅ ቀውስ ነበር፡፡ ለአስር ዓመት አገሪቱን ማፍያዎች የተቆጣጠሩበት ዘመን ነበር፡፡ ብዙዎቹ ከሶሻሊዝም መፈረካከስ በኋላ ሃያ ዓመትና ከዛ በላይ ወህኒቤት ታስረው የተለቀቁ ናቸው፡፡ ፓፓ ወይም ‹‹የማፍያ አባት›› በመባል የሚታወቁ ሲሆኑ ሁሉም በሥራቸው ሁለት መቶና ሶስት መቶ ሰዎች ያደራጃሉ፡፡ ከተማውን በሙሉ እነዚህ ሰዎች ተከፋፍለውት ነበር፡፡

በየሰፈሩ አንድ አንድ የሰፈር አለቃ ይኖራል፡፡ በአንደኛው ፓፓ ግዛት ሌላው ጣልቃ በመግባት ለመበጥበጥ ቢሞክር የሰፈር አለቆች አደብ ያስገዙታል፡፡ ማንኛውም በቢዝነስ ውስጥ የተሰማራ ሰው ለእነሱ በየወሩ የተጣለበትን ክፍያ (ደሞዝ) ይከፍላል፡፡ ማነው ክፍያውን የሚወስነው? ሚር X የተባለ የማፍያው ቡድን አለቃ (ፓፓ ይሉታል) የንግድ ቦታሽ ድረስ ይመጣና ‹‹ከማን ጋር ነው የምትሰሪው?›› ብሎ ይጠይቅሻል፡፡ (ከየትኛው የማፍያ ቡድን ጋር ማለቱ ነው) ስሙን መናገር አለብሽ፡፡

ፓፓ ከሌለሽ በየቀኑ ተመላልሶ የሚሸጠውን፣የሚወጣ የሚገባውን አይቶ፣ አጥንቶና ሰልሎ በወር 5ሺ ዶላር ወይም 10 ሺህ ዶላር ክፍያ ሊመድብብሽ ይችላል፡፡ በየወሩ የተመደበብሽን ገንዘብ ባትከፍይ ቤትሽ በቦንብ ሊፈነዳ ወይም በእሳት ሊቀጣጠል ይችላል፡፡ በጥይት ሊገሉሽም ይችላሉ፡፡ ማንም የሚደርስልሽ የለም፡፡ መንግስት የለም ማለት ነው? እንደሌለ ቁጠሪው፡፡ እነሱ ከመንግስትና ከፖሊስ ቁጥጥር ውጭ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ ነገሩ ሳይገባሽ ለፖሊስ ወይም ለመንግስት ብታመለክቺ ጥይት በጭንቅላትሽ ላይ ይለቁብሻል፡፡ አንዳንዴ ለምሳሌ--አንቺ ካዛንቺስ የምትሰሪ ከሆነ----የልደታው ፓፓ (ንጉስ) ይመጣና ‹‹ለእኔ ይሄን ያህል መክፈል አለብሽ›› ብሎ ይወስንብሻል፡፡ ያኔ የፓፓሽን ስም ትጠሪያለሽ--- ካመነሽ ይሄዳል፡፡ ካላመነ ‹‹ደውልልኝ በይው›› ብሎ ስልኩን ትቶ ይሄዳል፡፡ ተደዋውለው ‹‹የእኔ ነው›› ከተባባሉ ነገሩ በዚያው ያልቃል፡፡ በቃ አንቺ ጋ አይደርሱብሽም ማለት ነው ፤ ለአንደኛው ብቻ ትከፍያለሽ፡፡

በዚህ ዓይነት ቢዝነስ ማስፋፋት አስቸጋሪ አይሆንም? አዎ!! ቢዝነስሽ እየሰፋ ሲመጣ ቢዝነስ በከፈትሽበት ቦታ ሁሉ ችግር ይገጥምሻል ----እንደአዲስ ክፍያ መጠየቅሽ አይቀርም፡ ለፓፓሽ ታሳውቂና እነሱ ተነጋግረው ስምምነት ያደርጋሉ፡፡ ይኼ የአንቺ ጉዳይ አይደለም፡፡ “እኔ ግዛት ውስጥ የአንተ “ቢዝነስማን” መጥቶ ስለሚሠራ፣ለአንተ ከሚከፍልህ አስር ሺህ ዶላር ውስጥ ሁለት ሺ ዶላሩን ለእኔ ትከፍለኛለህ፣ የእኔ ግዛት ነው›› ተባብለው እነሱው ይስማማሉ፡፡ አንቺ ፓፓሽ የወሰነብሽን ብቻ ነው የምትከፍይው፡፡ ማፍያዎቹ በቢዝነሳችሁ የሚያግዟችሁ--- የሚሰሩላችሁ ነገር አለ? በሬስቶራንቱ ውስጥ ጉልቤ ወይም ዱርዬ መጥቶ ሂሳብ አልከፍልም ካለ ደውለን እንነግራቸዋለን፣ መጥተው አንገቱን አንቀው አስከፍለውት ይሄዳሉ፡፡ ሌላ ችግር እፈጥራለሁ የሚል ካለም አንዱ የማፍያ አባት ከሁለት መቶ እስከ ሶስት መቶ የሚደርሱ ወታደሮች ስላሉት ችግር የለም፡፡ መጥተው አፍንጫውን ሰብረውት ይዘውት ይሄዳሉ፡፡

የገባሻትን ቃል ከጠበቅሽ ለደህንነትሽ ስጋት የለብሽም፡፡ እኔ እና አንቺ ስንሰራ ለምሳሌ ‹‹ስጋ አቀርብልሃለሁ›› ብለሽ ከእኔ መቶ ሺህ ብር ብትወስጅና ብትክጂኝ “ለፓፓ” እንጂ ለመንግስት ወይም ለፖሊስ ሪፖርት አታደርጊም፡፡ ፓፓው ቤትሽ መጥቶ ‹‹ያደረግሽው ነገር ጥሩ አይደለም፤ የእኛን ልጅ ሃቅ አጥፍተሻል፤ ስለዚህ በሳምንት ጊዜ ውስጥ ሁለት መቶ ሺ ብር ታመጪያለሽ›› ተብሎ ይበየንብሻል፡፡ ቅጣት መሆኑ ነው? አዎ ቅጣት ነው፡፡ ‹‹ይሄን ባትፈፅሚ ልጅሽን አታገኚውም፤ ባልሽ ከስራ አይመጣም፤ አንቺም ላትኖሪ ትችያለሽ›› በማለት አስጠንቅቀውሽ ይሄዳሉ፡፡ ስለዚህ ከየትም ታመጫታለሽ፤ ክህደት የሚባል ነገር አይወዱም፡፡ ነገር ግን አንቺን ለማስጠቃት ሆን ብዬ “መቶ ሺ አበድሬው አልመለሰልኝም›› ብዬ ብዋሽና አጣርተው ቢደርሱበት በተመሳሳይ ቅጣቱ በእኔ ላይ ይጣላል፡፡

ህግ አስከባሪ ማፍያዎች ማለትም ይቻላላ ..? ህግ አስከባሪዎች ናቸው (ሳቅ) ለምሳሌ ለመንግስት መክፈል ያለብሽን ታክስ ካልከፈልሽ አይለቁሽም፡፡ የተከራየሽውን ቤት ኪራይ በወቅቱ መክፈልም አለብሽ፡፡ በቢዝነስ ሥራ ውስጥ ከመንግስት የሚጠበቅብኝን ሁሉ መፈፀም አለብኝ፡፡ ስንት የማፍያ አባቶች ነበርዎት፤ያሳለፉት ውጣ ውረድ ምን ይመስላል? ብዙ ውጣ ውረዶች ነበሩ፡፡ የአንድ ቀበሌ ማፍያ አለቃ ድንገት ይመጣና ‹‹የአንተን የማፍያ አለቃ አላውቅልህም፤ ለእኔ ትከፍለኛለህ፡፡ ለእኔ ካልከፈልከኝ በግንባርህ ጥይት ነው የምለቅብህ›› ብሎ ይሄዳል፡፡ ወይንም ደግሞ ‹‹ነገ ጠዋት መቶ ሺህ ብር ይዘህ እንድትመጣ፣ እዚህ ቦታ መጥቼ እወስዳለሁ›› ሊልሽ ይችላል፡፡ ይሄኔ ለፓፓሽ ደውለሽ ትነግሪዋለሽ፡፡ እሱም ወይ ችግሩን በቀላሉ ተነጋግሮ ይፈታዋል አሊያም ደግሞ “አውቃቸዋለሁ፤እነሱ ጭንቅላታቸውን ያማቸዋል፤ ከእነሱ ጋር ያለኝን ችግር እስክፈታ ከአካባቢው ዞር ብትይ ይሻላል›› ብለው ይመክሩሻል፡፡

ችግሩ እስኪፈታ መኖርያ ቤት መቀየር አለብሽ፡፡ ሶስት አራት ጊዜ እንዲህ ፈትነውኛል፡፡ አንድ ጊዜ ምን አጋጠመኝ መሰለሽ.. ‹‹ጋጊስታን›› የሚባሉት እቤቴ መጡና.. ጋጊስታን ምንድን ናቸው? ተባራሪ ማፍያዎች ናቸው፡፡ እኛ ጎንደር፣ ጎጃም፣ ወሎ፣ ባሌ..እንደምንለው በየክፍለአገሩ ይኖራሉ፡፡ ‹‹እኛ ክልል መጥተህ በመስራትህ ለእኛ መክፈል ይገባሃል›› ይሉኛል፡፡ ‹‹እኔ እኮ የእራሴ ሰው (ፓፓ) አለኝ--- ለምን አትነጋገሩም?›› አልኳቸው፡፡ ‹‹ያንተን ፓፓ አናውቅም! ትከፍላለህ ትከፍላለህ›› ብለው አፋጠጡኝ፡፡ ጉድ ፈላ! እንደነዚህ አይነት ማፍያዎች ከተለያየ ቦታ መጥተው ዘርፈው ነው የሚሄዱት፡፡ ተንቀሳቃሽ ናቸው፡፡ አንዴ ቦጭቀው ይሄዳሉ፡፡ ለፓፓዬ ደወልኩና ነገርኩት፡፡

‹‹አንተ ጋ መጡ?›› አለኝ፡፡ ፓፓዬ አውቋቸዋል፡፡ ‹‹አዎ›› አልኩት፡፡ ‹‹ሌላም የገደሉት ሰው ስላለ ችግሩን እስክፈታው ሌላ አካባቢ ሂድና ቤት ተከራይተህ ተቀመጥ›› አለኝ፡፡ ሶስት ወር ሌላ አካባቢ ሄጄ ተቀመጥኩ፡፡ እነሱ ሲፈላለጉ፣ ሲቀጣጠሩ፣ ሲነጋገሩ ቆዩ - ‹‹የእኛ ነው፤ የእናንተ አይደለም፡፡ እኛ ነን በፊት የምናውቀው…ከየት ነው ያገኛችሁት፤ እኔ ነኝ አባቱ፤ አይደለህም›› የሚለውን ከተነጋገሩ በኋላ አንድ ቀን መጡና ይዘውኝ ሄዱ፡፡ “ንግግራችን ላይ አንተ መገኘት አለብህ” ብለው ነው የወሰዱኝ፡፡ አንድ ትልቅ ሬስቶራንት ምድር ቤት ውስጥ ነበር ውይይታቸው የተካሄደው፡፡ እኔን መሃል አደረጉኝና በግራና በቀኝ ሃያ ሃያ ሆነው ተቀመጡ - ‹‹የእኔ ልጅ ነው፤ የእኔ ልጅ ነው›› ክርክር ያዙ፡፡ ‹‹እናንተ የእኔ አባት ልትሆኑ አትችሉም፡፡

የወለደኝ ለገሠ ደምሴ የሚባል አባት አለኝ›› አልኳቸው (ሳቅ) እነሱ ግን ‹‹እኔ ነኝ መጀመሪያ ያየሁት›› ማለታቸው ነው፡፡ ከዛ እኔን የሚጠይቁኝን ከጠየቁኝ በኋላ ‹‹ውጣ›› አሉኝ፡፡ ለእኔ ጠባቂ ሰጥተውኝ፤ታጅቤ መኪና ይዤ ስለነበር ተሰባሰቡና “ከእርሱ ፀጉር አንድ ፀጉር ብትወድቅ ነፍስ ይጠፋል፤እንዳትተኩሱ መኪናውን አስነስቶ ይሂድ” ብለው ተናገሩ፡፡ (ይሄ ሁሉ እንግዲህ በጠራራ ፀሐይ መንግስት ባለበት ነው የሚካሄደው) ጠቡ ወደ መታኮስ የሚያመራበት ጊዜ የለም…? ብዙ ጊዜ ማፍያዎች ሲጣሉ አካፋና መዶሻ መኪና ላይ ጭነው ወደ መቃብር ሥፍራ ነው የሚሄዱት፡፡ እዚያ ይተኳኮሳሉ፤ይገዳደላሉ፡፡ የተረፉት አካፋቸውን ከመኪና ላይ አውርደው የሞተውን ቀብረው ወደቤታቸው ይመለሳሉ፡፡ መቃብር ቦታ ከሄዱ ጠንከር ያለ ጠብ ተፈጥሯል ማለት ነው፡፡ እነዚህ ማፍያዎች ቤተሰብ፣ ልጆች--- ምናምን የላቸውም እንዴ? በህጋቸው መሠረት ማፍያ ሚስት የማግባት መብት የለውም፣ ንብረት ማፍራት አይችልም፤ ከእናት አባቱ ጋር መኖር አይችልም፡፡ ክልክል ነው፡፡ የውስጥ ህግና ደንብ አላቸው፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አዕዋፋት ተሰብስበው እያደኑ ስለሚይዟቸው ጠላቶቻቸው ይወያያሉ፤ አሉ፡፡ ዋና ሰብሳቢያቸው ንሥር ነው፡፡ ንሥር ያቀረበው ሃሳብ የሚከተለው ነበር፡- “እንደምታውቁት የምንወያየው የጠላቶቻችንን ፈሊጥ ተረድተን ራሳችንን ለማዳን ምን እናድርግ በሚለው ላይ ሲሆን ለዚህ አስፈፃሚ የሚሆነንን ተወካይ በመጨረሻ ለመምረጥ ነው፡፡ የምንመርጠው ተወካይ

1ኛ/ ባላንጣዎቻችን ጋ ሄዶ ማሳመን የሚችል

2ኛ/ለመወዳደርና ለመመረጥ አቅም ያለው

3ኛ/ከነሱ ጋር ተግባብቶ ውስጣቸውን ጥሩ አድርጐ ለማየትና ለኛ ሪፖርት ለማድረግ የሚችል

4ኛ/ በአደጋ ጊዜ ፈጥኖ ሊርቃቸውና ሊያመልጥ የሚችል መሆን ይኖርበታል፡፡

ሰብሳቢው ንሥር ባቀረበው ቅድመ - ሁኔታ ላይ ሁሉም ተስማሙ፡፡ በዚህም መሠረት የተለያዩ አዕዋፋት ለምርጫ ቀረቡና በከፍተኛ ድምጽ የተመረጠችው ቆቅ ሆነች፡፡ ቆቅም ባደረገችው ንግግር፤ “ወንድሞቼ እህቶቼ፤ አዕዋፋት ሆይ! እናንተን እወክል ዘንድ ስለመረጣችሁኝና ዕምነታችሁን ስለጣላችሁብኝ ከልብ የመነጨ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፡፡ እንደምታውቁት በአሁኑ ጊዜ መመረጥ ከፍተኛ ፈተና ያለበት ነው፡፡ ምክንያቱም፤ ሀ) ባላንጦቻችን ከመቼውም የላቀ አንድነት ያላቸው ሰዓት በመሆኑ፤ ለ) በውድድሩ እንድንሳተፍ ያደረጉን ተሳትፎ እንዲኖረንና ሌሎቹ ጫካ ነዋሪ እንስሳት ስለደግነታቸው እንዲያደንቋቸው ስለሆነ፤ ሐ) ወዳጅና ጠላታቸውን ለመለየት ቢያንስ ከእኛ አንዱ በመካከላቸው እንዲገኝ ብለው ስላሰቡ፤ ይመስለኛል። ሆኖም ካለመሳተፍ መሳተፍ የበለጠ ጥቅም ይኖረዋልና እናንተን መስዬ፤ እናንተን አክዬ እና እናንተን ሆኜ ለመቅረብ ዝግጁ ነኝ፡፡ ይህንንም ለማሳካት ሦስት ዘዴዎችን ለመጠቀም እሞክራለሁ፡፡

1ኛው ወቅታዊነት ነው፡፡ 2ኛው ከእነሱ የሰፋ አስተሳሰብ ይዞ፣ ቀድሞ መገኘት ነው፡፡ 3ኛው እነሱን አለመናቅና ሊበልጡኝ የሚችሉበት አንዳንድ ጉዳይ እንደሚኖር ማመን ነው፡፡ ሁሉም በቆቅ ሃሳብ ተስማሙና አጨበጨቡላት፡፡ በመጨረሻ እርግብ እንድትናገር እድል እንዲሰጣት ጠየቀች፡፡ ተፈቀደላት፡፡ እርግብም፤ “ወንድሞቼ፣ እህቶቼ አዕዋፋት ሆይ! ቆቅ በመመረጧ እንደማናችሁም በጣም ተደስቻለሁ፡፡ ሆኖም አንድ ቅር ያለኝ ነገር አለ፡፡ ይኸውም፤ ቆቅ፤ “ቆቅ” የሚለውን ስሟን ይዛ የትም አትደርስም የሚል ዕምነት ነው ያለኝ፡፡ ስለዚህ ስሟን ብትቀይር ጥሩ ነው እላለሁ፡፡ ማን እንበላት ካላችሁም እኔ “ዋ-ኔ” የሚል ስም ቢሰጣት መልካም ነው እላለሁ አለች፡፡” ሁሉም መስማማታቸውን በክንፋቸው በማጨብጨብ ገለፁ፡፡ እርግብም ቀጥላ “አሁን የሚያዋጣን ዛሬ ከባላንጦቻችን መወዳጀት ነው” አለች፡፡ “ለነገስ?” ብለው ጠየቋት፡፡ “ለነገማ የሆዳቸውን ስናውቅ እንወስናለን!” አለች፡፡

*** ከጥበብ ሁሉ የሚልቀው ወቅትን ማወቅ ነው፡፡ ወቅትን አለማወቅ አቅምን ካለማወቅ እኩል ነው፡፡ “እያንዳንዱ ድል አንድ አንድ ጠላት እንደሚወልድ አትርሳ” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ ስለዚህም አሸነፍኩ ብሎ ዘራፍ ማለት ከመሸነፍ አንድ የሚሆንበት ጊዜ አለ፡፡ ድልን በማጭበርበር የምንቀዳጅ ከሆነም ዕድሜ ልካችንን እንቅልፍ እንዳይወስደን ያደርገናል፡፡ ፖለቲካ ብዙው እጁ ሸፍጥ ነው፡፡ ሁኔታዎችን ለራስ እንደሚመች ለማድረግ ማናቸውንም ዘዴ መጠቀም ይጠይቃል፡፡ ደራሲና ፀሐፌ ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን በአንደኛው ቴያትሩ እንዳለው፤ “አብዮትኮ ኳስ ጨዋታ ነው፡፡ አቀበለ፣ ተቀበለ፣ ይዞ ሄደ - መታ - ፎሪ ወጣ፤ አብዮቱ ከሸፈ ይባላል፤ ወይም ቀጥሎ ደግሞ “ይዞ ሄደ! አብዶ ሰራ! መታ! - ጐል! አብዮቱ ግቡን መታ!! ይባላል፡፡

ይሄው ነው አብዮት ማለት - ኳስ ጨዋታ ነው፡፡ መቼ እንደምናቀብል፣ መቼ ወደፊት እንደምንሄድ፣ መቼ አብዶ (ምሣ) እንደምንሠራ ካላወቅን ፖለቲከኛ መሆን አንችልም፡፡ ይህንን ምንጊዜም መርሳት የለብንም፡፡ “የጐጃም ትውልድ በሙሉ ከአባይ እስከ አባይ” በሚለው መጽሐፉ፤ ደራሲ ግርማ ጌታኹን፣ እንዲህ ይላል … “ወለተ አልፋ አመተ አልፍን ወለደች፡፡ ከዚህ የሚአሳዝን ታሪክ አለበት፡፡ በአገር ላይ ያለ ወንድ ሁሉ በጦርነት አልቆ ወንድ ተወዶ ሳለ፤ ወለተ አልፋና ዓመተ አልፋ ዲማ ገበያ ሲሄዱ፣ ዝያ የሚባል ውሃ ሞልቶ አንድ ወንድ ጐዳነኛ ወስዶት ከዛፍ ላይ ሰቅሎት አዩ፡፡ “ሰው ነህ ግንድ” አሉት፡፡ እርሱ ግን የውርጭ ድደን ጥርሱን ገጥሞት መናገር ቸግሮት ነበርና ከዛፉ አውርደው ፀሐይ ቢአሞቁት፤ ዘመድ ላይ ከጃራ ሹም የመጣሁ ነበርሁ፡፡

ግን ውሃው አዋረደኝ ተፋኝ አለና ተናገረ፡፡ የዚህ ጊዜ እናትና ልጆች የኔ ባል ይሁን የኔ ባል ይሁን ተባባሉበት፡፡ ተያይዘው ከዲማ መነኮሳት ከነአባ ተጠምቀ መድኅንና ከነአባ ዮሐኒ ዘንድ ለፍርድ ሄዱ፡፡ እኒያም ሲፈርዱ አንች ባል አግብተሺ ቤት ሠርተሺ እርስዋን ወልደሻል፡፡ እርሷ ባል ሳታገባ ሳትወልድ ልታረጅ ነውና ለርስዋ ይሁን፡፡ አንች ብታገኝ አግቢ፤ ብታቂ መንኩሺና ተቀመጪ፣ ብለው ፈረዱ ይባላል፡፡” ወንድ ሁሉ ካገር የሚጠፋበት ዘመን አያድርስብን፡፡ እናትና ልጅ በአንድ ባል የሚጣሉበትን ጊዜ አይጣልብን! ድፍረትን ከሀፍረት ሳንነጥል የምናይበት ዐይን ይስጠን - በተለይ በምርጫ ወቅት፡፡ ዘራፍ ማለት፣ አለሁ አለሁ ማለት፣ ያለ እኔ ማን አለ ማለት፣ ካለፈው አለመማር፤ ከመርገምት ሁሉ የከፋ መርገምት ነው፡፡ ምንጊዜም ቢሆን፤ “የሚባለው ነብር ከጓዳ ሳይወጣ የሚበላው ፍየል ተክለፍልፎ መጣ” የሚለውን አገርኛ ግጥም አንርሣ!

የንባብ ባህልን ማበረታታት ዓላማው አድርጎ መጋቢት 7 ቀን 2002 ዓ.ም ፕሮግራሙን የጀመረው “ብራና” የሬዲዮ ፕሮግራም ሦስተኛ ዓመቱን ነገ በ8 ሰዓት በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ ሲያከብር፣የሙዚቃ ተመራማሪው አርቲስት ሠርፀ ፍሬስብሃት “ለንባብ ባህል መዳበር የመንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ሚና” በሚል ርእስ ጥናቱን ያቀርባል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት “የኢትዮጵያውያን የንባብ ልምድ በሀገር ውስጥና በባህር ማዶ” በሚል ርእስ አስተውሎቶቹን በቃለ ምልልስ መልክ እንደሚያቀርብ ይጠበቃል፡፡ በ “እናት ማስታወቂያ” እየተዘጋጀ በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 የሚቀርበው የሬዲዮ ዝግጅት ዘወትር እሁድ ከምሽቱ 2 ሰዓት እስከ 4 ሰዓት በሚተላለፈው እያንዳንዱ ዝግጅት ላይ ጥያቄ ለሚመልሱ 10 አድማጮች መፃሕፍት እየሸለመ መሆኑን አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡

*የወንድ ልጅ ብልት ቆርጠው “ተጫወችበት” ይላሉ--- *ቦንብ ታጥቀሽ ራስሽን አፈንጂ ተብዬ ነበር ---- *አፍሪካውያንን በኤሌክትሪክ ማቃጠል የተሰጠኝ የሥራ ኃላፊነት ነበር--- *ውሃ ስንጠይቅ ሽንታቸውን ነበር የሚሰጡን …እላያችን ላይ ይሸናሉ … ከአማርኛ ይልቅ አረብኛ መናገር ይቀናታል፡፡ የምትናገረው በቁጭት፣ በእልህና በፍርሃት ስሜት ነው፡፡ ከአራት ዓመት በፊት ለሥራ ወደ ሶሪያ የተጓዘችው ሃረግ (ሜሪ)፤ በሶርያ ከጦርነቱ መጀመር ጋር ተያይዞ ያሳለፈችውን መከራና ስቃይ በአንደበቷ ትናገራለች - አንዳንዴ በሰመመን፣ ሌላ ጊዜ በመንገሽገሽ፡፡ ከሶሪያ በሱዳን በኩል አድርጋ ወደ ኢትዮጵያ በገባች በአምስተኛ ቀኗ ከጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ጋር ያደረገችውን ቃለምልልስ ከዚህ በታች አቅርበነዋል፡፡ በሶርያ በምን ሥራ ላይ ነበር የተሰማራሽው? በ2009 ዓ.ም ወደ ሶርያ የሄድኩት በአውሮፕላን ነበር፡፡ እንደሌሎች ሴት እህቶቼ የቤት ውስጥ ሥራ ሳይሆን እርሻ ላይ ነበር ሥራ ያገኘሁት፡፡ ሥራዬ የወይራ ፍሬ መልቀም እንዲሁም ሙዝ፣ ትፋህ፣ አትክልትና ፍራፍሬ መኮትኮት፣ ማጨድ፣ ወዘተ ነበር፡፡ አንድ አመት ሙሉ ብቻዬን ነው የሠራሁት፡፡ ሴት ነሽ--- እንዴት የእርሻ ሥራን ልትመርጪ ቻልሽ? በመጀመሪያም ወደ ሶሪያ ስሄድ ሰው ቤት እንደምቀጠር አልነበረም የተነገረኝ፡፡ እዚያ ስደርስም ወደ ገጠር ነው የተላኩት፡፡ በእርግጥ ግብርናውን ወድጄው ነበር፡፡ ግን የምኖርበት ሰውዬ በጣም አስቸገረኝ፡፡ የተቀጠርኩበት ቤት እናትና ልጅ ነበሩ፡፡ ልጁ ትልቅ ሰው ቢሆንም የአእምሮ ዘገምተኛ ነበር፡፡ እናቱ አሮጊት ናት፡፡ ልጅዬው በተደጋጋሚ ይዝትብኝ ነበር፡፡ አብረሽኝ ካልተኛሽ እያለ ያስጨንቀኛል፡፡ ምን ልበልሽ… በጣም ያሳቅቀኝ ነበር፡፡ እና ስራዬን ሰርቼ ወደ ቤት መመለስ እንደ ጦር ነበር የምፈራው፡፡ ይመታኛል፣ ይጎትተኛል፣ ይጎነትለኛል … አንድ ዓመት ሙሉ በእነዚህ ሰዎች ቤት በስቃይ ቆየሁ ፡፡ ምን ያህል ነበር የሚከፈልሽ? ከዚህ ስሄድ 125 ዶላር እንደሚከፈለኝ ነበር የተነገረኝ፡፡ እዛ ስደርስ ግን መቶ ዶላር ሆነ፡፡ እንዲያም ሆኖ አንድ ዓመት ሙሉ የሰራሁበትን ገንዘብ ከሰዎቹ አልተቀበልኩም፡፡ በቃ ጠፍቼ ነው … የሄድኩት፡፡ በየወሩ አልነበረም ደሞዝ፡፡ አንድ ዓመት ከስድስት ወር ከሰራሽ በኋላ ነው የሚከፍሉሽ፡፡ እንዴት ጠፋሽ? በእርሻው ቦታ ላይ ስሰራ ጎረቤታችን የሆነ አንድ መልካም ሰው ሁልጊዜ ሁኔታዬን ያይ ነበር፡፡ አንድ ቀን አናገረኝ፡፡ እኔም የሚደርስብኝን በደል ሁሉ አጫወትኩት፡፡ እዚህ ሰውዬ ቤት ስቀጠር ህፃን ልጅ አለው ተብዬ ነበር … ይመስለኛል ለሰውዬው ማረጋጊያና ስሜት መወጫ ነው የወሰዱኝ፡፡ እኔ ከሄድኩ በኋላ እናቱን ሌላ አገር ልኳቸው እኔ ብቻ ከእርሱ ጋር ቀረሁ፤ ለሦስት ወር ሁለታችን ብቻ ነበር፡፡ በየጊዜው ይደበድበኝ ነበር፡፡ በተደጋጋሚ በስለት አስፈራርቶ ደፍሮኛል፤ እ..ከዛ በጣም ታመምኩኝ፣ አርግዤ ነበር፡፡ ‹‹ፔሬዴ ቀርቷል፤ ሃኪም ቤት ውሰደኝ አሊያም ወደ አገሬ ላከኝ›› አልኩት፡፡ ‹‹እገልሻለሁ›› አለኝ፡፡ ስንት ቀን እየፈራሁ ዛፍ ላይ ወጥቼ ‹‹አልወርድም›› እለው ነበር፡፡ … ይሄን ሁሉ ይመለከት ነበር - ያ ጎረቤታችን ሰውዬ፡፡ በኋላ ‹‹ከተማ ወስጄሽ የውጪ ዜጎች ቤት ትቀጠሪያለሽ›› አለኝ፡፡ ጎረቤትሽ ማርገዝሽን ያውቅ ነበር? አውቋል፡፡ ወደ ከተማ ሊወስደኝ የተነሳሳው እኮ ይህንንም ሚስጢር አጫውቼው ነው፡፡ ከዚያም ‹‹ማርሊዬስ›› የሚባል ክርስቲያን አረቦች የሚሄዱበት ቤተክርስትያን ወስዶ ጣለኝ፡፡ እዚያ ችግሬን ነገርኳቸው - ለቤ/ክርስቲያኑ ቄስ፡፡ ሀሙስ፣ አርብና ቅዳሜ ለሦስት ቀን ቤተክርስትያን ውስጥ አሳደሩኝ፡፡ “እሁድ ነው ኢትዮጵያውያኖች የሚመጡት፤ ከእነርሱ ጋር ትገናኛለሽ” አሉኝ፡፡ እሁድ ዕለት ኢትዮጵያውያኖች መጡ - ብዙ ናቸው፡፡ የደረሰብኝን በሙሉ አጫወትኳቸው፡፡ ቅዳሴ እንኳን ሳያልቅ ነው ይዘውኝ ወደ ቤታቸው የሄዱት፡፡ አንድ እንደ ትልቅ እህቴ የማያት ሴት ነበረች … ለእሷ ምስጢሬን ሁሉ አጫወትኳት፡፡፡ ‹‹ምንም ችግር የለም›› አለችና ሃኪም ቤት ሄድን፡፡ አስመረመረችኝ -----የሁለት ወር ተኩል እርጉዝ ነሽ ተባልኩ፡፡ እዛ አገር ማስወረድ ክልክል ነው፡፡ እርጉዝ ከሆንሽ ወደ አገርሽ አይልኩሽም፡፡ ከተወለደ በኋላ ልጁን ነጥቀው ነው አንቺን ወደ አገርሽ የሚሰዱሽ፡፡ በጣም አስቸጋሪ ህይወት ነው፡፡ ብወልደውም ልጄን አይሰጡኝም፤ ለማስወረድ ደግሞ ገንዘብ አልነበረኝም … እስከ አምስት መቶ ዶላር ያስፈልጋል ፡፡ ያቺ እንደ ትልቅ እህቴ የማያት ልጅ የምታውቀውን ሰው አነጋግራልኝ፣ እሱ ረዳኝና ፅንሱን አቋረጥኩ፡፡ ልጆች በእስር ቤት ወልደው የሚያሳድጉ ኢትዮጵያውያኖች አሉ ይባላል … በርካታ ኢትዮጵያውያኖች፣ ኤርትራውያኖችም … አሉ፡፡ እኔ ፅንሱን ካቋረጥኩ በኋላ … ሁለት ሳምንት … እቤቷ አረፍኩ፡፡ ምናልባት ሰውዬውም የሚያፈላልገኝ ከሆነ በሚል … ሁለት ሳምንት ሙሉ ከቤት አልወጣሁም፡፡ ከሌሎች ኢትዮጵያውያኖች ጋር ተገናኘሽ … ደማስቆ ውስጥ ያሉ ኢትዮጵያውያኖች በሙሉ እርስ በርስ ይተዋወቃሉ፡፡ በሳምንት አንድ ቀን እሁድ እሁድ አንድ ላይ እንውላለን፣ ቡና ይፈላል፣ ተሰብስቦ እረፍት መውሰድ፣ መዝናናት የተለመደ ነው፡፡ ሴቶቹ ሰው ቤት ነው የሚሠሩት፡፡ ወንዶቹ ግን አይቀመጡም--- እዛ አገር የሚሄዱበት ምክንያት በቱርክ አድርገው ወደ ሌላ አገር ለመሻገር ነው፡፡ አንቺ ከዛ በኋላ ሌላ ሥራ አገኘሽ ወይስ----- ራሴ አማርጬ ሰው ቤት ተቀጠርኩ፡፡ ቋንቋ ስለማውቅ ችግር አልገጠመኝም፡፡ አሮጊትና ሽማግሌ ባልና ሚስቶች ቤት ተቀጥሬ መሥራት ጀመርኩ ፡፡ ይኸኛውስ ቤት ተስማማሽ? ምን ያህል ይከፈልሽ ነበር? መጀመሪያ ስገባ መቶ ሃምሳ ዶላር ነበር፡፡ በኋላ ሁለት መቶ ሃያ አምስት ዶላር ሆነልኝ፡፡ አሮጊቷ ከተኛችበት አትነሳም፡፡ 85 ዓመቷ ነበር -- እሷን አንስቼ አጥባለሁ፡፡ ፓምፐርስ (የሽንትና የሰገራ መቀበያ) እቀይርላታለሁ፡፡ … መርፌ አወጋግ ልጃቸው አሰልጥናኝ -- መርፌ እወጋቸው ነበር፡፡ እንደ ልጃቸው ነበር የሚያዩኝ፡፡ ልጆቻቸው ዩኤን ነው የሚሠሩት፡፡ የመጀመርያው ቤት ፓስፖርቴን ትቼው ስለወጣሁ እዛ ተመዝግቤ በዚያ ወረቀት ነበር የምጠቀመው፡፡ አሮጊቷ የዛሬ ዓመት ሞተች፡፡ ከዛ ሽማግሌው ልክ እንደ ሚስቱ ሆነ፡፡ እሱን ሳነሳ ስጥል … (95 ዓመቱ ነበር፡፡) ግን በጣም ጥሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ የቤቱ ሃላፊ እኔ ነበርኩ፡፡ በጣም ሀብታሞች ናቸው፡፡ መኪና አስመጪና ላኪ ነበሩ፡፡ ሴቷ ልጅ ነበረች የቤተሰቦቿን ሀብት የምታስተዳድረው፡፡ ምን ያህል ጊዜ ሰራሽ? አራት ዓመት ከ6 ወር አብሬአቸው ነበርኩ፡፡ ጦርነቱ ሲጀመር ሃብታሞች ስለሆኑ ሁሉን ነገር ትተውት ወጡ፡፡ በመሃል እኔ ቀረሁ፡፡ ልጅቷ ፓስፖርት ልታወጣልኝ በጣም ደክማልኛለች፤ ግን አልተሳካም፡፡ እና ቤቱን ለእኔ ጥለው ወደ ቤሩት ተሳፈሩ፡፡ አካባቢው በጣም አስቀያሚ ነበር፡፡ አሸባሪዎች እንደፈለጉ የሚገቡበት የሚወጡበት ቦታ ነበር፡፡ እዚያ መኖር እንደማልችል አውቄዋለሁ፡፡ የነበርኩባቸዉ ሰዎች ደግሞ ክርስቲያኖች ነበሩ፡፡ አሸባሪዎች ይፈልጓቸዉ ነበር፡፡ ያንን ትልቅ ቤት ጥለውልኝ ብቻዬን ተሸክሜው ስለቀረሁ ተጨነቅሁ … መወሰን ነበረብኝ፡፡ በርካታ ቤተክርስያኖች ተቃጥለዋል፡፡ ፈርሰዋል፡፡ የሚሸሸው ክርስቲያኑ ነው፡፡ ፓስፖርት ያለው ይሸሻል፡፡ ፓስፖርት ኖሮት ብር የሌለው ኢትዮጵያዊ አለ---ሁሉም መሸሽ ነው፡፡ እስር ቤት መግባትም አለ፡፡ እኔም እጣ ፋንታዬ ይሄው ሆነ፡፡ በእስር ቤት ውስጥ .. የነበረውን ሁኔታ ንገሪኝ? እስር ቤት አንድ ወር ተቀመጥኩ፡፡ እስር ቤት እኮ የገባሁት ልመጣ አካባቢ ነው ከዛ በፊት በአሸባሪዎች እጅ ወድቄ ስንት ነገር ደርሶብኛል..በአሁኑ ሰዓት በጣም በረዶ ነው፡፡ እስር ቤት አትበይው … ‹‹የምድር ጀሃነም›› ነው፡፡ እዚህ ካዛንቺስ ሆነሽ ፍንዳታ ከተሰማ ተነስተሽ መገናኛ ድረስ ነው የምትሮጪው፡፡ ትራንስፖርት የለም፣ ከተያዙ መያዝ ነው፤ የሚሞተውም ይሞታል፡፡ አሁን እኔ በወጣሁበት ሰዓት ከተማው ላይ ብዙም ጦርነት አልነበረም፡፡ ዳር ዳሩ ላይ ነበር፡፡ እኔ ደግሞ እንደ አቃቂ ባለ ከከተማው ዳር ነበር የምኖረው፡፡ ከደማስቆ ራቅ ይላል፡፡ በጣም ብዙ ኢትዮጵያውያን ሴቶች በሴተኛ አዳሪነት ይሠራሉ የሚባለው እውነት ነው? ወደው አይደለም ሴተኛ አዳሪ የሚሆኑት፡፡ ፓስፖርት የላቸውም፤ ሊቀጠሩ ሲሄዱ ፓስፖርት ይጠየቃሉ፡፡ ቀጣሪዋ ‹‹አልፈግሽም›› ብላ ልታባርራት ትችላለች ፡፡ መኖር፣ መብላት ስላለባቸው የግድ ለእንደዚህ ዓይነት ህይወት ይዳረጋሉ፤ እዚያ ደግሞ የኢትዮጵያ ቆንስላ የለም፤ ኤርትራውያን እንኳ ቆንስላ አላቸው፡፡ ኤርትራዊ ላይ አንድ ችግር ቢደርስበት ቆንስላው ወደተከራየው ቤቱ ይወስዳቸዋል፡፡ ኢትዮጵያውያን በጣም የሚያሳዝን ነው ኑሯቸው ፡፡ አሁን እንኳን ወደ አገራቸው መምጣት አቅቷቸው በየሜዳው ወድቀዋል፡፡ በጦርነቱ ቤቱ ሁሉ እየፈረሰ ነው፡፡ ተከራይተው የሚኖሩት ንብረታቸውን ማውጣት አልቻሉም፡፡ የሴቶች ህይወት … በቃ ይሄው ነው፡፡ ወደው አይደለም የገቡበት ---- ኢትዮጵያውያኖች ያ ባህል ኖሯቸው አይደለም፤ በችግር ነው፤ አማራጭ በማጣት፡፡ እስር ቤት ከመጣልሽ በፊት..በአሸባሪዎች እጅ ወደቅሽ? በጣም አሰቃቂ ነው … በአሸባሪዎች እጅ ላይ ወደቅሁኝ፡፡ /ሰውነቷ ይንቀጠቀጣል፣ ለደቂቃዎች በዝምታ ቆየች፤ አይኖቿ እንባ አቀረሩ …) አየሽ ሰውነቴን … (ትከሻዋ አካባቢ እያሳየችኝ … የተቃጠለ ገላ …) ምንድን ነው? ሲጋራ ተርኩሰውብኝ ነው … … አሸባሪዎቹ ናቸው እንዲህ ያደረጉኝ--- የት ነው የወሰዱሽ? ቢሄዱት የማያልቅ ምድር ቤት (Underground) አላቸው፡፡ ውስጥ ለውስጥ ተቆፍሮ … የቀለጠ ከተማ ነው፡፡ በአንድ አቅጣጫ ብቻ እንዳይመስልሽ … ወደ አምስትና ከዛም በላይ አቅጣጫ መግቢያ መውጭያ ያለው ነው … የታሰሩ ሰዎች የሚሰቃዩበት፣ የጦር መሳሪያ በየዓይነቱ በብዛት ያለበት … ኑሯቸውም እዛው ነው? አዎ፡፡ ሴቶችም ወንዶችም አሉ፡፡ ብዙ ጊዜ አሸባሪዎቹ አይወልዱም፡፡ ከወለዱ ግን የልጆቻቸው አስተዳደግ አሰቃቂ ነው፡፡ በፊት ለፊታቸው አንገት በቢላዋ እየተቀላ፤ እጅና ጣት እየተቆረጠ … ያንን እያዩ ነው የሚያድጉት፡፡ ወንዶችን በፊንጢጣቸው … ኤሌክትሪክ ይልኩባቸዋል፡፡ ሴቶችን ህፃናቱ ፊት ይደፍራሉ፡፡ … የ3 እና የ5 ዓመት ህፃናት እንዲያዩ እንዲለማመዱ ይገፋፏቸዋል፡፡ የአሸባሪዎቹ ሚስቶች እዚያው አሉ፡፡ እነርሱም ሰውን ያሰቃያሉ፡፡ ሴትን ሴት፤ ወንድን ወንድ ነው የሚያሰቃየው፡፡ ሚስቱ ካሰቃየችኝ በኋላ ‹‹አምጫት›› ብሎ ይደፍረኛል፡፡ ሱዳኖች፣ ናይጄሪያዎች፣ ሴኔጋሎች … ብዙ የአፍሪካ ዜጐች ነበሩ - የሚሰቃዩ፡፡ የተለያየ አደንዛዥ ዕፅ ይሰጡናል፤ በመርፌ የሚወጋ፣ የሚጨስ፣ የሚሸተት … በግዴታ ነበር፡፡ ከዚያ መጋረፍ ነው … ወንዶቹ ብልት ላይና ምላሳቸው ጫፍ ላይ ኤሌክትሪክ ያደርጉባቸዋል፡፡ እኔን … ቦንብ ታጥቀሽ ራስሽን ታጠፊያለሽ ብለውኝ ነበር፡፡ ‹‹ላ … ላ›› አልኳቸው፡፡ ከዛ … የደረሰብኝን ስቃይ … (ረጅም ትንፋሽ) እስቲ የደረሰብሽን ንገሪኝ … … በቃ ተይው ይቅር … (ለመሄድ ተነስታ ተመልሳ በማቅማማት ተቀመጠች) አይዞሽ ንገሪኝ … ስታወሪው ይሻልሻል … ለመናገር ይከብዳል፡፡ የወንድ ልጅን ብልት ቆርጠው አምጥተው “ተጫወችበት” ይላሉ--- በጣም … አስቀያሚ ነው … ተይኝ ባክሽ … በተደጋጋሚ ስትደፈሪ እርግዝና አልተፈጠረም? ሃሃ … (ሳቅ) የሚሰጡኝ መድሃኒትስ … አምፒሲሊን ይሁን … ምን ይሁን አላውቅም ግን ይሰጡኝ ነበር … ስለዚህ እርግዝና የለም፡፡ ስቃይ ሲበዛብሽ … ምንም አትይም … ቁጣ ወይ ደግሞ … “በቃ ራሴን አፈነዳለሁ” አልኳቸው:: ውይ ሳልነግርሽ … ምግብ የለም፣ ውሃ በምንጠይቅ ሰዓት ሽንታቸውን ነበር የሚሰጡን … ሲያሰኛቸው በገላችን ላይ ይሸናሉ፡፡ ትንሽ ውሃ በተለያዩ ማደንዘዣ ዕፆች ቀላቅለው ጠጡ ይሉናል ፡፡ ያን ከሰጡኝ በኋላ የሚያደርሱብኝ ስቃይ አይታወቀኝም … እና “አፈነዳለሁ” ብዬ ተስማማሁ … ወጥቼ ልሙት … አንድ ኢትዮጵያዊ ይህንን እንዳዳረገች ሁሉም ይወቅ ብዬ ወሰንኩ፡፡ ከእንግዲህ ምን ቀረኝ … ብሬን ንብረቴን ወስደውታል፡፡ አማርኛ የማወራው--- ችግሬን የማስረዳው ሰው እንኳን የለም፡፡ እንዲህ እናድርግ ምናምን ብላችሁ ከሌሎቹ ጋር አትማከሩም ነበር? እኔ ከሴቶች ጋር ሳይሆን ከወንዶች ጋር ነበር ይበልጥ የምቀራረበው፡፡ ናይጀሪያኖች፣ ሱዳኖች … ሱዳኖች በእኔ ስቃይ በጣም ተጐድተዋል … ስጮህ ይሳቀቁ ነበር፡፡ በእነሱ ፊት ይገናኙኝ ነበር፡፡ አፍሪካውያኖችን በኤሌክትሪክ አቃጥይ ይሉኝ ነበር፡፡ “ሂጅና አቃጥያቸው”፤ “ሽንትሽን ሽኝባቸው…” እባላለሁ፡፡ እነሱ ጋ ስደርስ በጣም አለቅስ ነበር፡፡ ጣታቸውን … እግራቸውን ይቆርጡባቸዋል፡፡ … ህክምና የለ፤ ደማቸው እየፈሰሰ ነው የሚውሉት … አቃተኝ (ረጅም ትንፋሽ) ምን ያህል ነበሩ? አስራ ሶስት፡፡ ከሞቱት ሌላ ማለቴ ነው---- (ደረትዋን ደጋግማ በእጅዋ ትይዛለች) አቤት ...ሽታው በልብሴ ...በሠራ አካላቴ ጠረኑ ሁሉ..ይመጣብኛል፡፡ ናይጀራዊው ጋ ሄጄ የታዘዝኩትን ስነግረው ..በአረብኛ ‹‹..አድርጊው..ካላደረግሽው አትወጪም፤ እኛንም አታድኝንም..አድርጊው..ለኩሽኝ..›› አለኝ፡፡ አልቻልኩም፤ የመጀመሪያ የጨካኝነት ልምምድ ነበር፡፡ አለቀስኩኝ፡፡ በብዛት ኮኬን እወስድ ነበር፡፡ ስትለኩሺያቸው ቆመው ያዩሽ ነበር? አዎ.. ደስ ይላቸዋል፡፡ .ናይጀሪያዊውን እየለኮስኩት ሳለ “ጭኔ ላይ የምታያት የበር ቁልፍ ናት፡፡ እቺን ይዘሽ መውጣት ትችያለሽ” አለኝ፡፡ እሱን እየለኮስኩ ቁልፉን ወሰድኩት፡፡ አረቡ እያየን አልነበረም፡፡ ናይጄሪያዊው ቁልፉን ከየት አገኘው? ከየት እንዳገኘው መጠየቅም አልፈለኩም፤ ጊዜውም አልነበረኝም፡፡ ማውራት አንችልም ነበር፤ ከናይጀሪያዊው ጋር ልንግባባ የምንችለው በአረብኛ ቋንቋ ብቻ ነው፡፡ በንግግርሽ ውስጥ እንግሊዝኛ ከሰሙ ...ጉድሽ ነው፡፡ የተለየ ቋንቋ እንድትናገሪ አይፈቀድልሽም፡፡ (ንግግርዋን አቋርጣ) ይቅር በለኝ--- አሰቃየኋቸው፡፡ በኤሌክትሪክ ከለኮስኳቸው በኋላ ስላለቀስኩ ..‹‹ለምን ታለቅሻለሽ›› ብለው አሰቃዩኝ፡፡ ‹‹የገነት ፓስፓርት›› የሚሉት አለ፡፡ የገነት ፓስፖርት ... ሰው ገድለው ገነት የሚገቡበት ፓስፖርት፡፡ የራሳቸው የቡድን ፓስፖርት ነው፡፡ ‹‹ነፍስ አጠፋለሁ›› ብዬ ስነሳ ፓስፖርት ተሰራልኝ፡፡ ፓስፖርቱ ምን አለው? ምንም፡፡ የእኔ ስምና የቤተሰቤ ስም ዝርዝር አለው፡፡ አረንጓዴ ነው፡፡ ፎቶ የለውም፡፡ ስትገልጪው ይሄ ብቻ ነው የያዘው መረጃ፡፡ “የገነት ፓስፖርት” ይላል ፅሁፉ፡፡ ፓስፖርቴ ተሰራልኝ፡፡ እላዬ ላይ ቦንብ ካጠመዱልኝ በኋላ የገነት መግቢያ ፓስፓርቴም፣ አብሮ ይታተምልኛል፡፡ ፓስፖርቴ ተሰራ፤ አብሬያቸው እሰግድ ነበር፤ ቁራን እንዴት እንደሚቀራ አስተማሩኝ፡፡ “የዛሬ 15 ቀን ወደ ገነት መሄጃሽ ነው ማረፍ አለብሽ” ብለው ነገሩኝ... እረፍቱ የት ነው …? ‹‹የምድር እረፍት›› ነው የሚሉት፡፡ 15 ቀኑን የሟች ሬሳ በተጠራቀመበት … (ፀጥ አለች) … ሰውነታቸው የተቆራረጠ ሰዎች በብዛት ተገድለው በተጣሉበት … ከነበርንበት ወደ አንድ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ … ሬሳ ውስጥ … ከሙታን ጋር፡፡ ጨካኝ … እንድትሆኝ ነው … እዚያ የጉድጓድ መውጫ በር አለ … ያ … ናይጄሪያዊ የሰጠኝ ቁልፍ መውጫ ነው … እሱ እኮ ከታሰረ ሁለት ዓመቱ ነው … ጦርነቱ ሲጀምር የተያዘ ነው፡፡ እረፍት እንደሚወስዱኝ ሁሉ ያውቃል፡፡ … በዚያ አሰቃቂና ዘግናኝ ቦታ በአጋጣሚ ህይወቱ ያላለፈ ትኩስ ቁስለኛ … (የገደሉት መስሏቸው ትተውት የሄዱት) አገኘሁ፡፡ ለመሞት ጥቂት ደቂቃዎች ነበር የቀረው፡፡ የእረፍቱ ቦታ..... ሱሪ እና አሮጌ ነገር አለበሱኝ፤ ሬሳው ውስጥ ተቀመጥኩ፡፡ … እፀልይ ነበር … ቁልፉን እንዴት ይዘሽው ገባሽ? በማህፀኔ ውስጥ ደብቄ … በምኔም ልደብቅ አልችልም ነበር፡፡ ስፀልይ ሰውየውም ቀና አለ … እጅግ ያሳዝናል … ሰውነቱ ሁሉ የተጠባበሰ ነው … ተበለሻሽቷል፡፡ ይህ ሰው እንደተጋደመ “ሬሳዎቹን … ገለል ገለል አድርገሽ ውጪ” ብሎ አሳየኝ … የደረጃ መወጣጫ … አለው … እሱ ሲወጣ አስፓልት ይገኛል፡፡ እየመጡ አያዩሽም ነበር? በፍፁም አያዩኝም … 15 ቀን ካረፍኩ በኋላ መጥተው ይወስዱኛል … ብቅ ብለው ግን አያዩኝም፡፡ ከዛ ሰው ጋር ተግባባሁ፤ ውሃ … ሲለኝ ሽንቴን ሸንቼ ሰጠሁት፡፡ ህይወቱን ለትንሽ አተረፍኩት፡፡ … በሌሊት በሩን ከፈትን … ተሸክሜ … አወጣሁና ጣልኩት፡፡ እነሱ ለሊት ለሊት ስራ አይሰሩም፡፡ ስራቸው ቀን ነው፡፡ በግርግር ጫጫታ ባለበት ሰዓት እንጂ … ጨለማ ተገን አድርገው እንኳን ሰውን አይደበድቡም፡፡ ቢያስተጋባ ቢሰማብን ብለው ስለሚያስቡ ይፈራሉ፡፡ ሌሊት መጠጣት ነው ሥራቸው፡፡ የቆሻሻ ቱቦ … ስር ለስር … የትና የት የሚደርስ--- ውስጥ ለውስጥ የሚያስኬድ መንገድ መሰለሽ … እንደ ምንም ደረጃውን ተሸክሜው … እየጎተትኩት … ወጥተን ያ ናይጄሪያዊ በሰጠኝ የበለዘ ቁልፍ … ከፈትኩት … ስወጣ አስፓልት ላይ ነው የወጣሁት፡፡ ቅርብ ነው ለከተማው፡፡ ምሽት ላይ ነበር፤ ማንም ዝር አይልም፡፡ ‹‹ስምርዬ›› የሚባል ቦታ አለ፡፡ እንደ አውቶብስ ተራ ዓይነት ነው፡፡ አስፓልቱ ላይ ከወጣን በኋላ … ተሸክሜ ያወጣሁት ሰው … የተወሰነ ቦታ ድረስ እየጎተትኩት ከተማ አካባቢ ስንደርስ አደባባይ ላይ ጥዬው ሄድኩ፡፡ ከወጣሁ በኋላ ደክሞኛል … አሞኛል፡፡ ኢትዮጵያኖችን መጠጋት አልቻልኩም፡፡ ለምን? በጣም አስቀያሚ ሁኔታ ላይ ነበርኩ፡፡ ሀሺሽ ጠጥቻለሁ፣ ጠረኔ በጣም መጥፎ ነው፤ ፀባዬ ከፍቷል፡፡ በዛ ሰዓት የሄድኩት ቤተክርስቲያን ነው፡፡ ፀለይኩ … አለቀስኩ … የት እንደምሄድ አላውቅም፡፡ … ሁሉ ነገር ብርቅ ሆኖብኛል፡፡ መንገድ ላይ ስዘዋወር አንድ ኢትዮጵያዊ አገኘሁ፡፡ ሳናግረው “ሰምተናል ሰምተናል” አለኝ፡፡ ምኑን? አንዲት ኢትዮጵያዊ ተይዛለች መባሉን፡፡ ማን እንደሆነች ግን አላወቅንም ነበር፡፡ በአሸባሪዎች እጅ ወደቀች ሲባል ሰምተናል - አለኝ፡፡ በአገሪቱ ላይ ስልክ የሚባል የለም … አጋጣሚ ሆኖ በነጋታው ወደ ካናዳ የሚሳፈር ልጅ ነበር፤ በጣም አዘነ፡፡ ከዛ ጉድጓድ ከወጣሁ በኋላ ግን በጣም ፈራሁ … የሚያየኝ ሰው ሁሉ የሚያውቀኝ የሚከተለኝ… የሚገለኝ ይመስለኝ ነበር፡፡ ቀን ቀን ስታያቸው ኖሮማል ሰው ስለሚመስሉ፤ ለብሰው ዘንጠው ስለሆነ የሚወጡት … አንድ ሰው አስተውሎ ካየኝ ከእነርሱ መካከል አንዱ ይመስለኝ ነበር፡፡ በአጋጣሚ በዛን ወቅት ደግሞ በዊግ ቁጥርጥር ተሰርቻለሁ … በፀጉሬ ይለዩኛል ብዬ እሰጋም ነበር፡፡ “እባክህ ከአንድ ሱናዳዊና ናይጄሪያዊ የተሰጠኝ መልዕክት አለ … ስማቸው እገሌ ይባላል … ሂጂና ያሉበትን ቦታ ተናገሪ ስላሉኝ እዛ ውሰደኝ” አልኩት፡፡ ናይጄሪያዎች በጣም ጎበዞች ናቸው … እንዴት እንደሚወጣ … ያውቃሉ ----ጥበበኞች ናቸው እና ይሄን ልንገር አልኩት፡፡ የተባለው ቦታ ወሰደኝ፡፡ ... ነገርኳቸው፡፡ ተላቀስን -- ቁልፍ ሰጥቶ ያስወጣኝ የናይጄርያው ወንድም “ኢሾ” ይባላል፡፡ ምን ማድረግ እንዳለብን አወራን፡፡ ቦታው እንደዚህ ዓይነት ቦታ ነው፤ ቁልፉም ይሄው … ‹‹ስጪያቸው እነርሱ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ያውቃሉ ነው ያለኝ” አልኩት፡፡ ቁልፉ ላይ … ሌላ መልዕክት አለው? እንዴ … እንዴት አወቅሽ? --- ቁልፉ ሰፋ ያለ ነው.. በላዩ ላይ በራሳቸው ቋንቋ ፅፈውበታል … ሰጠኋቸውና አወጣጤን ነገርኩት፡፡ አለቀሱ፤ በህይወት የለም ብለው ደምድመው ነበር፡፡ (እንባዋን እየጠረገች) አንድ ኢትዮጵያዊ ከአንድ ሱዳናዊ ጋር አገናኘኝ፡፡ በጣም ባለውለታዬ ነው-- እንደ ነገ ወደ ካናዳ በረራ ነበረው--- ለእኔ ሲል ቀኑን አራዘመ … በሃሺሽና በተለያዩ ሱሶች የተበከለው ደሜ … ባህሪዬን አስከፍቶት ስለነበረ መርዙ ከደሜ እስኪወጣ ድረስ ተቸገርኩ፡፡ ስለዚህ … አስመረመረኝ … ከሰው ጋር ትንሽ ትራቅና ትቀመጥ ተባለ … መድሃኒት ተሰጠኝ፡፡ ያ ያስተዋወቀኝ ያልኩሽ ሰው በሱዳን አድርጌ ወደ ኢትዮጵያ እንድመጣ ነገሮችን ያመቻችልኝ ጀመር፡፡ ሌላ ዳዊት ባህሩ የሚባል ኢትዮጵያዊ (እዛ የሚኖር የአሜሪካ ዜግነት ያለው) … የቻልኩትን ሁሉ እረዳታለሁ … ፓስፖርቷንም በማውቀው ሰው አወጣላታለሁ አለ፡፡ የምንኖረው አንድ አፓርታማ ላይ ነው፡፡ እኔን ይዞ ሲወጣ ሲገባ ያየ ሰው በትኩረት ያየኝ ነበር፡፡ ስወጣ ከእግር ጥፍሬ እስከ ራስ ፀጉሬ ተከናንቤ ነበር የምወጣው፡፡ እዛ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደግሞ አይከናነቡም፡፡ ‹‹አሸባሪ ናት፤ ጥቁር ናት ግን ተከናንባ ነው የምናያት ፈራናት›› ብለው አስጠቆሙኝና እስር ቤት ገባሁ፡፡ የዩኤን ወረቀት ነበረኝ፡፡ የደረሰብኝን ነገር ሁሉ አጫወትኳቸው፡፡ እስር ቤት ውስጥ ስገባ ለእኔ እረፍት ነበር፤ አልተጐዳሁም፡፡ ከእስር ቤት ውጪ ያሉ ኢትዮጵያውያን በየሜዳውና በየመናፈሻው ወዳድቀው ተወንጫፊና፣ ተፈንጣሪ መሳሪያ እየወደቀባቸው ይሞታሉ፡፡ እኔ በቅርብ የማውቃት ልጅ የሞተች አለች፡፡ እኔ እዚህ ስመጣ … አሁንም የሚያስለቅሰኝ እዛ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ሁኔታ ነው … ቢያንስ መቶ ኢትዮጵያውያንን ማምጣት ቢቻል ---

በጉብዝናህ ወራት የመጦሪያህን ነገር አስብ! ከድሬዳዋ ጅቡቲ መንገደኞችንና ለንግድ ሥራ የሚንቀሳቀሱ ኮንትሮባንድ ነጋዴዎችን የሚያመላልሰው ባቡር የዘወትር ደንበኛ ነበሩ፡፡ በድሬዳዋ ከተማም እኔ ነኝ ያሉ እውቅ የኮንትሮባንድ ነጋዴ በመሆናቸው ወ/ሮ ፋጡማ ሮብሌን የማያውቅ የድሬዳዋ ከተማ ነዋሪ አልነበረም፡፡ በወጣትነትና በጐልማሳነት የዕድሜ ዘመናቸው ከፊናንስ ወታደሮች እየደበቁ፣ አንዳንዴም እየተሻረኩ ደህና ጥሪት ለመያዝ ችለው ነበር፡፡ የኮንትሮባንድ ንግዱ ከጉምሩክ ፍተሻ ሲያልፍ አትራፊ፣ በኬላ ላይ በሚደረግ ፍተሻ ሲወረስ ደግሞ እጅግ አክሣሪ መሆኑን ቀድሞውኑ ያውቁ ነበርና በየጊዜው የሚያጋጥማቸው ነገር ሣይረብሻቸው ለዓመታት በዚሁ ንግድ ዘለቁ፡፡ የኩባንያ ሠራተኛ የነበሩት ባለቤታቸው በሞት ስለተለዩዋቸውና ሰባቱን ልጆቻቸውን የማሣደጉና የማስተማሩ ኃላፊነት በእሣቸው ትከሻ ላይ ብቻ በመውደቁ፣ ቀን ከሌት ሣይሉ የሚባትሉ ትጉህ ነጋዴ ነበሩ፡፡

በኮንትሮባንድ ንግዱ ላይ የሚደረገው ፍተሻና ቁጥጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጠነከረ ሲሄድ ሁሉም ነገር እንደቀድሞው ቀላል አልሆንላቸው አለ፡፡ በደካማ አቅማቸው እሣት ከላሱ ነጋዴዎች እየተጫረቱ የሚያመጡትን ልባሽ ጨርቆች ኬላ ላይ የፊናንስ ወታደሮች ያስቀሩባቸው ጀመር፡፡ ለምግብ እንጂ ለሥራ ያልደረሱት ልጆቻቸው ይህንን የእናታቸውን ችግር ለመረዳት የሚችሉበት ዕድሜ ላይ አልነበሩምና ችግራቸውን ለብቻቸው ለመወጣት መፍጨርጨራቸውን ቀጠሉ፡፡ ጨከን ብለው የኮንትሮባንድ ንግዱን ጥለው ወደ ሌላ ሥራ እንዳይሰማሩ አልችለውም የሚል ሥጋት ያዛቸው፡፡ ምን አድርጌ? …እኔ … ከልጅነት እስከ ዕውቀት ሥሠራው የኖርኩትና የማውቀው ሥራ ይህንኑ ብቻ ነው፡፡ ሌላ ሥራ አላውቅ፡፡ ጭንቀቱ ፈተናቸው፡፡ እስኪ ትንሽ ቀን … ነገ ምን እንደሚመጣ ማን ያውቃል … ተስፋቸውን ሰንቀው ጥረታቸውን ቀጠሉ፡፡ አንዴም ሲያስከፋ አንዴም ሲያስደስታቸው የኖረው የኮንትሮባንድ ንግድ፤ ከቀናቶች በአንደኛው ቀን የመኖር ተስፋቸውን የሚያጨልምና ህይወታቸውን አደጋ ላይ የሚጥል አጋጣሚ ፈጠረባቸው፡፡

ከድሬዳዋ ጅቡቲ መንገደኞችን አሣፍሮ ይጓዝ የነበረው ባቡር በመገልበጡ፣ በባቡሩ ላይ ተሳፍረው ከነበሩት መንገደኞች አብዛኛዎቹ የሞትና ከባድ የመቁሰል አደጋ ደረሰባቸው፡፡ እንደ ዕድል ሆነናም ወ/ሮ ፋጡማ በአደጋው ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው ከሞት ከተረፉት መንገደኞች መካከል አንዷ ሆኑ፡፡ ሁኔታው እጅግ አሣዛኝ ነበር፡፡ በአደጋው በወ/ሮ ፋጡማ እግሮችና እጆች ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡ እነዚያ ሮጠው የማይጠግቡት እግሮቻቸው ያለ ድጋፍ አልንቀሣቀስ አሏቸው፡፡ የሰው እጅ አላይም ብለው ሲታትሩ የኖሩት እናት፤ አካል ጉዳተኝነት ከቤት አዋላቸው፡፡ የወ/ሮ ፋጡማን ቤት ችግር ገባው፡፡ ልጆች ኑሮን ለመቋቋም አቅም አጡ፡፡ ህይወት ፈተና ሆነችባቸው፡፡ የወ/ሮ ፋጡማ ልጆች ይህንን የህይወት ፈተና እንደ እናታቸው ተጋፍጠው ለመቋቋም የሚያስችላቸውን አቅም አላገኙም፡፡ ቀስ እያሉ ከፈተናው እየወደቁ ቀሩ፡፡ ከወለዷቸው ሰባት ልጆቻቸው መካከል ደካማና ህመምተኛ እናትን የመጦርና የመንከባከብ፣ ታናናሽ እህትና ወንድሞችን የማስተማርና የማሣደግ ኃላፊነትን ለመወጣት የሚችል ልጅ ማግኘት የማይቻል ሆነባቸው፡፡

የሚሆነውን ሁሉ አልጋ ላይ ሆነው ከማየት የዘለለ ነገር የማድረግ አቅም አጡ፡፡ እነዛ የነገን ተስፋ የሰነቁባቸው፣ ተምረውና አድገው ይጦሩኛል ያሏቸውና ያለ አባት ያሣደጓቸው ሰባት ልጆቻቸው በየተራ ይህቺን ዓለም እየተሰናበቷት ሔዱና እናታቸውን ብቸኛ አደረጓቸው፡፡ ህይወት ይብስ ጨለመች፡፡ ሰባት ልጆቻቸውን ሞት የነጠቃቸውን እናት፤ ከልጆቻቸው መካከል አንደኛዋ አያት አድርጋቸው ነበርና ከዚሁ ህፃን ጋር ኦና ቤታቸውን ታቅፈው ቀሩ፡፡ እንደ ቀድሞው እዚህም እዚያም ብለው ሠርተው መኖር ባለመቻላቸው ቤታቸው የሚላስ የሚቀመስ ነገር ጠፋ፡፡ ይህንን ሁኔታ የተረዱት የአካባቢያቸው ሰዎች እዛው ድሬዳዋ ከተማ ውስጥ ወደሚገኘው “ዳዊት የአረጋውያን መጦሪያ ድርጅት” እንዲሄዱ መከሩአቸው፡፡ ወደ ድርጅቱ ሲመጡም የእሳቸው ዓይነት እጣ ፈንታ የገጠማቸውን በርካታ አረጋውያን በማየታቸው እንደገና የመኖር ተስፋቸው ለመለመ፡፡ ወ/ሮ ፋጡማ ዛሬ በማዕከሉ በየቀኑ ለቁርስ ብቻ የምትሰጣቸውን ምግብ ለመቀበል ማልደው እያነከሱ ወደ ማዕከሉ ይመጣሉ፡፡

ይህቺኑ ከድርጅቱ የምትሰጣቸውን ምግብ ከሚያሣድጉት የልጃቸው ልጅ ጋር እየተቃመሱና ለነፍስ ያሉ በጐ አድራጊ ግለሰቦች በሚያደርጉላቸው የአልባሳት እርዳታ ህይወታቸውን እየገፉ ይገኛሉ፡፡ እኚህን እናት ያገኘኋቸው Help age Ethiopia የተባለ ድርጅት ሰሞኑን በድሬዳዋ ከተማ ውስጥ የሚገኙ ሁለት የአረጋውያን መርጃ ማዕከላትን ባስጐበኘን ወቅት ሲሆን ወ/ሮ ፋጡማ በዳዊት የአረጋውያን መረጃ ማዕከል ውስጥ የሚረዱ እናት ናቸው፡፡ አሰገደች አስፋው የአረጋውያን መረጃ ማዕከልም በጉብኝት ፕሮግራሙ በጋዜጠኞች የተጐበኘ የአረጋውያን መረጃ ማዕከል ነው፡፡ ሁለቱም ማዕከላት በግለሰቦች የራስ ተነሳሽነት የተቋቋሙ ቢሆንም ለአረጋውያኑ የእርዳታ አገልግሎት የሚሰጡት በተለያዩ መንገዶች ነው፡፡ ወ/ሮ ፋጡማ ሮብሌን ያገኘሁበት “ዳዊት የአረጋውያን መርጃ ማዕከል” ለአረጋውያኑ እርዳታና እንክብካቤ የሚያደርገው አረጋውያኑ በመኖሪያ ቦታቸዉ ላይ ሆነው በየዕለቱ ጠዋት አንድ ጊዜ የምግብ አገልግሎት በመስጠት ሲሆን ህክምናና አልፎ አልፎ ደግሞ የአልባሣት ድጋፍም ያደርግላቸዋል፡፡ በወ/ሮ አሰገደች አስፋው መጦሪያ ማዕከል ውስጥ ያየኋቸው አረጋውያን ግን ሙሉ ኑሮአቸው በዚሁ ድርጅት ውስጥ ሆኖ፣ በቀን ሦስት ጊዜ ምግብ እየተመገቡ የቀንና የሌሊት ልብስ ተሰጥቶአቸው ህክምናም እንዲያገኙ እየተደረገ ነው፡፡

በሁለቱም የአረጋውያን መጦሪያ ማዕከላት ዘር፣ ሃይማኖትና ብሔር ቦታ የላቸውም፡፡ 950 አረጋውያን የሚረዱበት የ“ዳዊት አረጋውያን መርጃ ማዕከል” ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዳዊት በቀለ እንደነገሩን፤ ማዕከሉ ከተለያዩ በጐ አድራጊ ድርጅቶች የሚያገኘውን እርዳታ ለእነዚህ አረጋውያን እንዲደርሳቸው ያደርጋል፡፡ አረጋውያኑን ከአንድ ጊዜ በላይ ለመመገብ የማዕከሉ አቅም አለመፍቀዱን ተነግሮናል፡፡ ከማዕከሉ እርዳታ ከሚያገኙት አረጋውያን ብዙዎቹ ልጆቻቸው በህይወት የሌሉና እጅግ ከፍተኛ በሆነ የድህነት ህይወት ውስጥ ያሉ ናቸው፡፡ በማዕከሉ ውስጥ የኤች አይ ቪ ኤድስ ህሙማንም አግኝተናል፡፡ እነዚህ አረጋውያን ከዕድሜያቸው መግፋት በተጨማሪ በሽታው ባስከተለባቸው አዕምሮአዊና አካላዊ ህመም ሣቢያ እንደ ልባቸው ተሯሩጠው የዕለት ጉርሳቸውን ማግኘት አይችሉም፡፡ ማዕከሉ ደግሞ የሚሰጣቸው በቀን አንድ ጊዜ ለቁርስ የምትሆን ሩዝ፣ ዳቦ ወይም ቅንጬ ብቻ ነው፡፡

ይህ በቂና ተመጣጣኝ ምግብ ማግኘት ለሚገባው የኤች አይቪ ኤድስ ታማሚ የሚበቃ አይደለም፡፡ ሆኖም አረጋውያኑ በዚህች ብቻ ለመኖር ተገደዋል፡፡ ሰዓቱን ጠብቆ መወሰድ የሚገባውን መድሃኒት ለመውሰድ አረጋውያኑ ምግብ እስኪሰጣቸው አይጠብቁም፡፡ በባዶ ሆዳቸው ይውጡታል፡፡ ይህ ደግሞ ዕድሜ፣ ረሀብና በሽታ ያደከማቸው አረጋውያን አንጀት የሚችለው አይደለም፡፡ ይህንን ሁኔታ ማዕከሉ ታሳቢ አድርጐ በተለይ ለኤች አይቪ ህሙማን የተለየ እንክብካቤና ድጋፍ ሊያደርግላቸው ይገባል የሚል እምነት አለን፡፡ ሌላው በዳዊት የአረጋውን መርጃ ማዕከል ውስጥ ያገኘናቸው አዛውንቶች ትልቅ ችግር የመኖሪያ ቤት እጦት ነው፡፡ አብዛኛዎቹ አረጋውያን ወደ ማዕከሉ የሚመጡት ልጆቻቸውን ወይም ቤተሰቦቻቸውን በሞት ሲነጠቁና ጧሪና ረዳት ሲያጡ ነው፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ከመኖሪያ ቤታቸው ተፈናቅለው በየእምነት ተቋማቱ ደጃፍ እና በየጐዳው ላይ የወደቁ አረጋውያን ቁጥር በርካታ ነው፡፡ በዳዊት የአረጋውያን መርጃ ማዕከል ውስጥ ያገኘኋቸው ተረጂ አረጋውያን እንዳጫወቱኝ፤ በቅርቡ ሁለት የዚህ ማዕከል ተረጂ የነበሩ አዛውንቶች በጅብ የመበላት ክፉ እጣ ገጥሟቸዋል፡፡ ይህ እጣ ፈንታ በሌሎችም በእድሜ በገፉና ጧሪና ቀባሪ ባጡ አረጋውያን ላይ የማይደርስበት ምክንያት የለም፡፡ ሌላው በድሬዳዋ ከተማ ውስጥ አረጋውያንን ሰብስቦ እርዳታና ድጋፍ የሚያደርግላቸው ማዕከል የወ/ሮ አሰገደች አስፋው የአረጋውያን መጦሪያ ማዕከል ነው፡፡

በአንዲት እናት በጐ ፈቃደኝነት የተቋቋመው ማዕከሉ፤ ዛሬ አንድ መቶ ሰላሳ ረዳትና ደጋፊ የሌላቸውን አረጋውያን ሰብስቦ ይጦራል፡፡ ሰማንያ የሚደርሱትን ደግሞ እዚያው በመኖሪያ ቤታቸው ውስጥ እርዳታ እያደረገላቸው ይገኛል፡፡ የድርጅቱ መስራች ወ/ሮ አሰገደች አስፋው፤ የሞላ ቤት ንብረታቸውን ሸጠው፣ ወርቅና ጌጣቸውን በገንዘብ ለውጠው አረጋውያኑን ወደ መጦርና መንከባከቡ ሥራ ሲገቡ “አበደች” ያላላቸው ሰው አልነበረም፡፡ ከልጅነታቸው ጀምሮ እድሜያቸው የገፉ ሰዎችን መርዳትና መንከባከብ፣ የተቸገሩን ማገዝ ደስታ ከሚሰጧቸው ተግባራት መካከል ዋንኞቹ ነበሩ፡፡ ይህ በልጅነት እድሜ የተጀመረው ያጡትን የመርዳትና የመደገፍ ፍላጐት እድሜያቸው ከፍ እያለ ሲሄድ አልተዋቸውም፣ እንደውም ሀብትና ንብረትን አስንቆ ከአረጋውያንና ከደካማ ሰዎች ጋር አብሮ መኖር ይበልጥ ደስታ እንዲሰጣቸው አደረጋቸዉ እንጂ፡፡ ልጆቻቸው ከአገር ውጪ ቢሆኑም በእናታቸው ሀሳብና ስራ ላይ ተቃውሞ የላቸውም፡፡ ይልቁንም አቅማቸው በፈቀደ መጠን እናታቸውን ለማገዝ ጥረት ያደርጋሉ፡፡ ይህን የወ/ሮ አሰገደችን ብርቱ ጥረትና ቀና ተግባር የተመለከተው የአለማያ ዩኒቨርሲቲም ለወ/ሮ አሰገደች ሰባት የወተት ላሞችን በእርዳታ ሰጣቸው፡፡ እርዳታና ድጋፍ አድርጉልኝ ማለት የማይሆንላቸው እኚህ ሴት፤ ከብቶቹ ገቢ ለማስገኘት እንዲችሉና በራሳቸው ገቢ ለመተዳደር እንዲበቁ ጥረት ማድረጋቸውን ቀጠሉ፡፡ የአረጋውያን መጦሪያ ማዕከሉን ባቋቋሙበት የተንጣለለ ሜዳ ላይ የጓሮ አትክልቶችንና የፍራፍሬ እርሻዎችን ማልማት ጀመሩ፡፡

ከእርሻ የሚያገኙትን ፍራፍሬ ለገበያ በማቅረብ እና ከወተት ላሞቹ ከሚገኘው የወተት ምርት ሽያጭ የሚገኘው ገቢ የወ/ሮ አሰገደችን ሀሳብ ከግብ ለማድረስ አቅም ሆናቸው፡፡ “እኛ እርዳታና ልመና አናውቅም ሠርተን እንኖራለን፡፡ የድሬዳዋ ህዝብ ደግሞ ደግ ነው፡፡ ተለይቶንም አያውቅ፡፡ ሁሌም ከጎናችን ነው” የሚሉት ወ/ሮ አሰገደች፤ ዛሬ ለማዕከሉ ገቢ ማስገኛ የሚሆን የሚከራይ ህንፃ በመገንባት ላይ ናቸው፡፡ ለስራ እንጂ ለወሬ እምብዛም ቦታ የማይሰጡት ወ/ሮ አሰገደች፤ ስለማዕከሉና ስለሚሰጡት እንክብካቤና ድጋፍ ብዙ መናገር አይፈልጉም፡፡ “እኔ ያደረግሁት ነገር የለም፡፡ ሁሉም በፈጣሪና በድሬዳዋ ህዝብ የሆነ ነው፡፡” የሚል ነው ምላሻቸው፡፡ እዚሁ መጦሪያ ማዕከል ውስጥ አግኝቼ ያነጋገርኳቸው አቶ አድነው ሸዋረጋ የተባሉ የ78 አዛውንት ወደዚህ ማዕከል ከመጡ ሶስት አመት እንደሆናቸው አጫውተውኛል፡፡ በማዕከሉ የሚደረግላቸውን እንክብካቤና ድጋፍ አስመልክተው ሲናገሩ፤ “እኔ ቃል የለኝም፡፡ በህይወቴ ሁሉ ከኖርኩባቸዉ ጊዜያት እዚህ ማዕከል ውስጥ ያሳለፍኩት ሦስት አመታት እጅግ የተለዩና አስደሳች ነበሩ፡፡ ንፁህ በልቼ ንፁህ ለብሼና ንፁህ መኝታ ላይ ተኝቼ እየኖርኩ ነው፡፡ የወጣትነትና የጉልምስና ዘመኔን የኖርኩት ወደፊት ምን ያጋጥመኛል የሚል ስጋትና ሀሳብ ሳይኖርብኝ ነው፤አስቤውም አላውቅም ነበር፤ ለካ ጌታ ይሄን አዘጋጅቶልኝ ነው፡፡ ልጆች አልወለድኩም፡፡

ግን ጧሪና ተንከባካቢ እግዚአብሔር ሰጥቶኛል” ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ከሚኖሩት አራት ሚሊዮን አረጋውያን መካከል አብዛኛዎቹ እጅግ በከፋ ድህነትና ችግር ውስጥ እንደሚኖሩ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚ/ር በቅርቡ ይፋ ያደረገው መረጃ ያመለክታል፡፡ ከእነዚህ አረጋውያን መካከል መደበኛ ወርሃዊ የጡረታ ገቢ የሚያገኙት 500ሺ ያህሉ ብቻ እንደሆኑና ቀሪዎቹ አረጋውያን ከቅርብ ዘመዶቻቸውና ቤተሰቦቻቸው በሚያገኙት ጥቂት ገንዘብ እንደሚተዳደሩ መረጃው ይጠቁማል፡፡ አረጋውያኑ ከተተኪው ትውልድ ክብርና እንክብካቤ የማግኘታቸው ሁኔታ በእጅጉ እየቀነሰ መምጣቱን የጠቆመው መረጃው፤ ለዚህም ምክንያቱ አረጋውያንን የመጦር ባህልና ወግ መሸርሸሩና ቤተሰባዊ ትስስሩ እየላላ መምጣቱ ዋንኞቹ ናቸው ይላል፡፡ አረጋውያን ረዳትና ደጋፊ እንዲያጡ ከሚያደርጓቸው ሌሎች ምክንያቶች መካከል ስደትና ኤች አይ ቪ ኤድስ እንደሚገኙባቸው የጠቆመው መረጃው ፤ ከተለያዩ አካባቢዎች ስራና ትምህርት ፍለጋ ወደ ዋና ከተሞች የሚፈልሱ ወጣቶች አዛውንት ወላጆቻቸውን ለከፋ ድህነትና ረጂ አልባነት እንደሚዳርጓቸው አመልክቷል፡፡

ትኩስ የወጣትነት ጉልበትና ብሩህ አእምሯቸውን ለሀገራቸውና ለወገናቸው ዕድገትና መሻሻል ሲገብሩ ኖረው የዕድሜ ጀምበራቸው ስታዘቀዝቅ፣ ጉልበታቸው ሲደክም፣ ጧሪና ተንከባካቢ ሲያስፈልጋቸው፣ ጀርባችንን ልንሰጣቸው አይገባንም፡፡ እነዚህ ሁለት በግለሰቦች ተነሳሽነት የተቋቋሙት የአረጋውያን መርጃ ማዕከላት በስፋት ሊሰራባቸውና በሁሉም ክልሎች ተግባራዊ ሊሆኑ ይገባል፡፡ መንግስትም ሆነ ዜጎች ለጉዳዩ ተገቢውን ትኩረት ሊሰጡት ያሻል፡፡ የዛሬው ወጣት የነገ አረጋዊ መሆኑ አይቀርምና በጉብዝና ወራት የመጦሪያን ነገር ማሰቡም ተገቢ ነው፡፡