Administrator

Administrator

“ለልጆቻችን ደህንነት ለማይጨነቁ ልበቢሶች ነው የሰራሁት” ካናዳዊው ኮሜዲያን ጂም ኬሪ የጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን ለመቃወም “ኮልድ ዴድ ሃንድ” የተሰኘ የሙዚቃ ቪድዮ በመስራት እንዳሰራጨ ተገለፀ፡፡ “ፈኒ ኦር ዳይ” በተባለ ድረገፅ የተለቀቀውን ይሄን ክሊፕ ከአንድ ሚሊዮን በላይ ሰው እንደተመለከተው የዘገበው ፎክስ ኒውስ፤ በኮሜዲያኑ ላይም ከፍተኛ ትችት እንደቀረበበት ጠቁሟል፡፡ ጂም ኬሪ ከአራት ዓመት በፊት ህይወቱ ያለፈውን የቀድሞ ተዋናይ እና የ“ናሽናል ራይፍልስ አሶሴሽን” ፕሬዝዳንት የነበረውን ቻርልስ ሄስተን ገፀባህርይ በመላበስ በካንትሪ ስልት ሙዚቃውን ተጫውቷል፡፡ በክሊፑ ላይ ጆን ሌነን፤ ማህተመ ጋንዲ እና አብርሃም ሊንከልንም ተተውነዋል፡፡

እስከ 10 ሚሊዮን የሚደርሱ አድናቂዎቹ በሚከታተሉት የትዊተር ማስታወሻው ላይ ጂም ኬሪ በፃፈው መልእክት፤ የሙዚቃ ቪድዮውን ለልጆቻችን ደህንነት ለማይጨነቁ ልበቢሶች ነው የሰራሁት ብሏል፡፡ በአሜሪካ ጦር መሳርያ የመታጠቅ መብት እንዲታገድ መጠነ ሰፊ ቅስቀሳ ሲካሄድ ቢሰነብትም ጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን የሚከለክል ህግ እንዲወጣ የሚደረገው ጥረት ስኬታማ መሆኑ ያጠራጥራል እየተባለ ነው፡፡ የኒውዮርክ ከንቲባ ማይክል ብሉምበርግ እስከ 12 ሚሊዮን ዶላር በጀት ይዘው የፀረ ጦር መሳርያ እንቅስቃሴ እያካሄዱ መሆኑን የዘገበው ብሉምበርግ ኒውስ ፤ በተቃራኒው በአሜሪካ መንግስት ከፍተኛ ተፅእኖ ያላቸው 15 ዴሞክራት እና ሪፐብሊካን ሴናተሮች የጦር መሳርያ የመታጠቅ መብትን ለመከልከል የተያዘውን ዘመቻ በይፋ እየተቃወሙ እንደሆነ አመልክቷል፡፡ ከ32 በላይ ፊልሞችን የሰራውና በመላው አለም እስከ 2.4 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ገቢ ያስገባው ኮሜዲያን ጂም ኬሪ ፤ ቢያንስ 12 ያህል ፊልሞቹ ከ100 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ እንዳስገኙለት ይታወቃል፡፡

የብሪታኒያ ተዋናዮች በሆሊውድ ፊልም ሰሪዎች ተመራጭ እና ተፈላጊ እየሆኑ መምጣታቸውን ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር አስታወቀ፡፡ በማራኪ የእንግሊዘኛ ቋንቋ አነጋገር፤ በምርጥ የትወና ብቃታቸው፤እንዲሁም በሚጠይቁት ተመጣጣኝ ክፍያ የእንግሊዝ ተዋናዮች ተመራጭ ሆነዋል ተብሏል፡፡ በበርካታ የሆሊውድ ፊልሞች መሪ ተዋናይነት በመስራት እና በመልመል አሜሪካውያኑን ከገበያ እያስወጡ እንደሆነም ዘ ሆሊውድ ሪፖርተር ዘግቧል፡፡

የእንግሊዝ ምርጥ የትወና ብቃት በሲኒማ ብቻ ሳይሆን በቲቪ ተከታታይ ፊልሞችም እየታየ ሲሆን በአሜሪካ የቴሌቭዥን ጣቢያዎች በአሜሪካውያን ህይወት ላይ የሚያጠነጥኑ ፊልሞች ላይ ሳይቀሩ እንግሊዛውያኑ በብዛት እየተወኑ ነው፡፡ የታላቋ ብሪታኒያ የፊልም ኢንዱስትሪ 100ኛ ዓመት ክብረ በዓል ከወር በኋላ ንግስት ኤልዛቤት በሚገኙበት እንደሚከበር የገለፀው ዘጋርድያን፤ በዚሁ ስነስርዓት ላይ በሆሊውድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያገኙ የብሪታኒያ ምርጥ ተዋናዮች ይመሰገናሉ ብሏል፡፡

ድሮ ድሮ በሆሊውድ ፊልሞች የመጥፎ ገፀባህርያት ሚና ይሰጣቸው የነበሩ የብሪታኒያ ተዋናዮች፤ ከቅርብ አመታት ወዲህ ግን በከፍተኛ በጀት በተሰሩ፤ ታሪካዊ ይዘት ባላቸው እና በሱፐር ሂሮ ፊልሞች ላይ መተወን ይዘዋል፡፡ በሆሊውድ የእንግሊዞቹ ዋና ተፎካካሪዎቻቸው አውስትራሊያውያን ብቻ እንደሆኑም ታውቋል፡፡ አንቶኒ ሆፕኪንስ፤ ማይክል ኬን፤ ጋሪ ኦልድማን፤ ሲን ኮነሪ፤ሁውጅ ግራንት፤ራልፍ ፊነስ በሆሊውድ በግንባር ቀደምነት የሚጠቀሱ የእንግሊዝ ተዋናዮች ናቸው፡፡

በ“ሊንከለን” ፊልም ላይ የተወነው እንግሊዛዊው የፊልም ባለሙያ ዳንኤል ዴይ ሊውስ ለሶስተኛ ጊዜ በምርጥ ተዋናይነት የዘንድሮን ኦስካር በመውሰድ ሪከርድ ያስመዘገበ ሲሆን ባለፉት አምስት ዓመታት ከአምስት በላይ የብሪታኒያ ተዋናዮች የኦስካር ሽልማቶችን እንደወሰዱ ይታወቃል፡፡ 2013 ከገባ ወዲህ ክርስትያን ቤል፤ጃሬድ ሃሪስ፤ ዳንኤል ዴይ ሊውስ፤ ኢድሪስ ኤባ እና ሌሎች እንግሊዛውያን ተዋናዮች በምርጥ የሆሊውድ ፊልሞች ላይ በመሪ ተዋናይነት በመተወን ተወዳዳሪ አልተገኘላቸውም፡፡

የሊል ዋይኔ አዲስ አልበም ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ 2›› በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ለገበያ የቀረበ ሲሆን ሽያጩ እንደሚደራለት ከወዲሁ ተገምቷል፡፡ ከሳምንት በፊት ሊል ዋይኔ ከድንገተኛ የልብ ህመም ጋር በተገናኘ በገጠመው የጤና እክል ከሞት አፋፍ እንደተረፈ ተዘግቧል፡፡ በማህበረሰብ ድረገፆች አነጋጋሪ በመሆን በአንድ ሳምንት ውስጥ ከቀድሞው የ19ኛ ደረጃ ወደ ሁለተኛ ደረጃ የተመነደገው ራፐሩ፤ አጋጣሚው ለአዲሱ አልበሙ ጥሩ ማሻሻጫ ይሆንለታል ተብሏል፡፡ ራፐሩ ከሚወስደው ሃይል ሰጭ መጠጥ ጋር በተያያዘ ለህይወቱ የሚያሳስብ አደገኛ ደረጃ ላይ ደርሶ እንደነበረ ያወሱት ዘገባዎች ፤ ሆስፒታል ገብቶ በተደረገለት ከፍተኛ የህክምና ክትትል ህይወቱ እንደተረፈ ጠቁመዋል፡፡ ሊል ዋይኔ የገጠመው የጤና እክል ከጭንቀት ጋር በተያያዘ የተፈጠረ እንጅ በአደገኛ እፅ ተጠቃሚነት አለመሆኑን ያስተባበለው የአሳታሚው “ካሽ መኒ” ስራ አስኪያጅ ፤ በቂ እረፍት በመውሰድና ራሱን በማዝናናት ጤንነቱ እንደሚመለስለት ተናግሯል፡፡

ከ2013 ምርጥ አልበሞች አንዱ እንደሚሆን ተስፋ የተጣለበት የሊል ዋይኔ አዲስ አልበም በከፍተኛ ጉጉት ሲጠበቅ እንደቆየ የዘገበው ሮሊንግ ስቶን መፅሄት፤ በአልበሙ ላይ ኒኪ ማንጅ፤ ድሬክ፤ ቢግ ሲን፤ ገን ፕሌይ እና ሌሎች ራፐሮች በአጃቢነት እንደሰሩ አመልክቷል፡፡ የአልበሙን ሽፋን ምስል የሰራለት የሂፖፕ ሙዚቀኛው ካናዬ ዌስት እንደሆነ የገለፀው መፅሄቱ ፤ ሊል ዋይኔ የዓለም ምርጥ ራፐር መሆኑን ካናዬ መመስከሩንም ጨምሮ አስታውቋል፡፡ ራፐሩ ከሁለት ዓመት በፊት ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ›› በሚል ስያሜ የመጀመርያውን የአልበሙን ክፍል ለገበያ እንዳበቃ የሚታወስ ነው፡፡ ሊል ዋይኔ ከአዲሱ አልበሙ ‹‹አይ አም ኖት ኤ ሂውማን ቢንግ 2›› በኋላ አጠቃላይ የስራዎቹን ብዛት 11 ያደረሰ ሲሆን በሙዚቃ ህይወቱ 95 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ሃብት ማፍራቱን ለማወቅ ተችሏል፡፡

Saturday, 30 March 2013 16:03

አዳዲስ ፊልሞች

አዲስ አበባ የሚገኘው የብራዚል ኤምባሲ ዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ ያዘጋጀውና ከየካቲት 22 ጀምሮ ሲካሄድ የሰነበተው የብራዚል የባህል ፌስቲቫል ነገ በኤምባሲው በሚቀርብ የሙዚቃ ዝግጅት ይጠናቀቃል፡፡ የካቲት 22 ቀን 2005 ዓ.ም ሸራተን አዲስ በሼፍ ክርስቲያኖ ላና፤ በሸራተን አዲስ በቀረበና ለስምንት ቀናት በዘለቀ የምግብ ፌስቲቫል የተጀመረው ዝግጅት፤ ከመጋቢት 2 እስከ መጋቢት 7 በቆየ የፊልም ፌስቲቫለ የቀጠለ ሲሆን “The Passion of Brazilian Football” በሚል ርእስ መጋቢት 11 የጀመረው የፎቶግራፍ አውደርእይም ዛሬ ይዘጋል፡፡ የኤምባሲው አንደኛ ፀሐፊ እና የባህል አታሼ ሚስተር ማርሴሎ ቦርሄስ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ዛሬ ማታ በኤምባሲው የሚደረገውን መዝጊያ ፊደል የሙዚቃ ባንድ ያቀርባል፡፡

ታላቁን የኢትዮጵያ የዜማ አባት ቅዱስ ያሬድ 1500ኛ ልደት ምክንያት በማድረግ የተዘጋጀ የህይወት ታሪኩን እና ሥራዎቹን የተመለከተ መፅሐፍ ታተመ። በአቶ ታደሰ አለማየሁ የተዘጋጀው ባለ 202 ገፆች መፅሐፍ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምርያ ማህበረ ቅዱሳን አሳትሞ እያከፋፈለው ነው፡፡ ይኸው መፅሐፍ ዛሬ ከቀኑ 8 ሰዓት በብሔራዊ ቤተመዘክር ትልቁ አዳራሽ እንደሚመረቅ ከማህበሩ የተገኘው መግለጫ ያስረዳል። በመፅሐፉ ውስጥ ከተካተቱ ርእሰ ጉዳዮች መካከል የዘፈን እና የመዝሙር ልዩነትን ይመለከታል፡፡ የመፅሐፉ ዋጋ 50 ብር ነው፡፡

Saturday, 30 March 2013 15:30

ኃይሌ በ40 ዓመቱ ይሮጣል

በሃዋሳ በስሙ የሚያዘጋጀው ማራቶን ትኩረት እያገኘ ነው በቅርቡ 40ኛ ዓመቱን የሚይዘው ኃይሌ ገብረስላሴ በ “ግሬት ማንችስተር ራን” እንደሚሳተፍ የውድድሩ አዘጋጆች አስታወቁ፡፡ ስለተሳትፎው የተጠየቀው ኃይሌ ‹‹ሩጫ ስለሚያስደስትኝ መሮጤን እቀጥላለሁ፤ መቼ እንደሚያበቃልኝ አላውቀውም፤ ወደ ማንችስተር ተመልሼ ለመወዳደር የምችልበትን እድል መተው አልችልም›› ብሏል፡፡ ኃይሌ በ “ግሬት ማንችስተር ራን” የ10 ኪሎሜትር ሩጫ ለ6 ጊዜያት ሲያንፍ፤ ላለፉት አምስት ተከታታይ ዓመታት የውድድሩ አሸናፊ ነበር፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ዘንድሮ “ኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን” በሃዋሳ ከተማ መካሄዱ ትኩረት እየሳበ ነው፡፡ የውድድሩ አምባሳደር አትሌት ኃይሌ ገብረስላሴ ለተሳታፊዎች ባቀረበው በጥሪ ለ20 ዓመታት ካሳለፈው የሩጫ ዘመን በኋላ ዓለምን ወደ አገሩ ኢትዮጵያ ሲጋብዝ በታላቅ ጉጉት እንደሆነ ገልጿል፡፡

የኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን በኢትዮጵያ በአውሮፓ እና በአሜሪካ ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የውድድር አዘጋጆች በተሰባሰቡበት ቡድን የሚመራ ሲሆን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀና ቀለሙ ኢትዮጵያዊ ማራቶን ነው ተብሏል፡፡ ከ1200 በላይ ተሳታፊዎች እንደሚኖሩት ከሚጠበቀው ኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ጋር በመያያዝ የግማሽ ማራቶን፤ የ5 ኪሎሜትር የጎዳና ላይ ሩጫ እና የህፃናት ውድድሮችም ይደረጋሉ፡፡በውድድሩ ኦፊሴላዊ ድረገፅ በቀረበው መረጃ መሰረት በኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ተሳታፊ ለሚሆኑ ራጮች የጉብኝት ፕሮግራም የተዘጋጀ ሲሆን የኢትዮጵያን ባህልና ታሪክ ለማስተዋወቅ ታስቧል፡፡ የኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን ጋር ተያይዞ በሚደረገው የገቢ ማሰባሰብ 200ሺ ዶላር ለእንጦጦ ፋውንዴሽን እንደሚበረከትም ታውቋል፡፡ በኃይሌ ገብረስላሴ ማራቶን በሁለቱም ፆታዎች ለሚያሸንፉ አትሌቶች ለእያንዳንዳቸው 12 ወቄት ወርቅ ይሸለማል፡፡

ለውድድሩ መሮጫ የተመረጠችው የሃዋሳ ከተማ ከዓለም አቀፉ የአማተር አትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ጋር በሚደረግ ትብብር በቀጣይ ወራት የእውቅና ሰርተፍኬት ለውድድሩ አዘጋጅነት ይሰጣታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በተያያዘ ዜና ባለፈው ሳምንት በፖላንዷ ከተማ ባይድጎስዝ በተደረገው 40ኛው የዓለም አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ኬንያ 5 ወርቅ በማግኘት ስኬታማ ስትሆን ኢትዮጵያ በግልና በቡድን 10 ሜዳልያዎች በመሰብሰብ ከፍተኛ ውጤት አስመዘገበች፡፡ በሻምፒዮናው አጠቃላይ የውጤት ሰንጠረዥ ኬንያ 5 ወርቅ፤ 3 ብርና 1 ነሐስ በመውሰድ አንደኛ ሆና ጨርሳለች፡፡ ኢትዮጵያ በ3 የወርቅ፤ 4 የብርና 3 የነሐስ ሜዳልያዎች በማግኘት ሁለተኛ ሆና በሻምፒዮናው በአዋቂ ወንዶች 12 ኪሎ ሜትር፤ በአዋቂ ሴቶች ስምንት ኪሎ ሜትር እንዲሀም በወጣት ሴቶች የ4 ኪሎ ሜትር ውድድሮች ኬንያውያን የወርቅ ሜዳልያዎችን በመሰብሰብ ውጤታማ ሆነዋል፡፡

የኢትዮጵያው አትሌት ሃጎስ ገብረ ህይወት በወጣት ወንዶች 6 ኪሎ ሜትር ብቸኛውን የወርቅ ሜዳልያ ድል አስመዝግቧል፡፡ ከ32 አገራት የተወከሉ 102 አትሌቶች በተሳተፉበት የአዋቂ ወንዶች 12 ኪሎ ሜትር ውድድር በቡድን ውጤት ኢትዮጵያ 1ኛ ደረጃ ስትወስድ አሜሪካና ኢትዮጵያ ተከታታዩን ደረጃ ወስደዋል፡፡ ከ29 አገራት የተወከሉ 97 አትሌቶች በተሳተፉበት የአዋቂ ሴቶች 8 ኪሎ ሜትር ውድድር ደግሞ በቡድን ውጤት ኬንያ 1ኛ ደረጃ ስትወስድ ኢትዮጵያና ባህሬን ተከታታዩን ደረጃ ወስደዋል፡፡

ባለፈው ሳምንት በአዲስ አበባ ስታዲየም በዓለም ዋንጫ የሶስተኛ ዙር የማጣሪያ ጨዋታ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የቦትስዋና አቻውን 1ለ0 በማሸነፍ የምድቡን መሪነት አጠናከረ፡፡ ዋልያዎቹ በዚሁ ጨዋታ ከቦትስዋና ያልጠበቁት ከባድ ፉክክር የገጠማቸው ሲሆን ብቸኛዋን የማሸነፊያ ጎል ባለቀ ሰዓት የደደቢቱ ጌታነህ ከበደ አስቆጥሮ ሙሉ ሶስት ነጥብ ሊመዘገብ ችሏል፡፡ በሌላ የምድብ 1 ጨዋታ መካከለኛው አፍሪካ ሪፖብሊክን በኬፕታውን ያስተናገደችው ደቡብ አፍሪካ 2ለ0 አሸንፋለች፡፡

ከዓለም ዋንጫ የሶስተኛ ዙር የማጣሪያ ጨዋታ በኋላ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በ7 ነጥብ እና በ3 የግብ ክፍያ መሪነቱን ማስጠበቅ የቻለ ሲሆን ደቡብ አፍሪካ በ5 ነጥብ ሁለተኛ ደረጃን ይዛለች፡፡ ከሶስተኛ ዙር የማጣሪያ ጨዋታ በፊት ሁለተኛ ደረጃ ላይ የነበረችው መካከለኛው አፍሪካ በደቡብ አፍሪካ ከተሸነፈች በኋላ በሶስት ነጥብ ወደ ሶስተኛ ደረጃ ስትወርድ በኢትዮጵያ የተሸነፈችው ቦትስዋና በአንድ ነጥብ በነበረችበት የመጨረሻ ደረጃ ላይ ረግታለች፡፡

ኢትዮጵያ በምድብ 1 በሁለት ነጥብ ልዩነት መሪነቷን መቀጠሏ ወደ ዓለም ዋንጫው የማለፍ ተስፋ ካላቸው ቡድኖች ተርታ እንዳሰለፋት በተለያዩ ዘገባዎች ተገልጿል፡፡ በተመሳሳይ ዲ.ሪፖብሊክ ኮንጎ፤ አይቬሪኮስት፤ ካሜሮን፤ ሴኔጋልና ቱኒዝያ በየምድባቸው መሪነት ጉዟቸውን በስኬት ቀጥለዋል፡፡ በ2014 ብራዚል ለምታስተናግደው 20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ የሚደረገው የምድብ ማጣርያ በአራተኛ ዙር ከ4 ወራት በኋላ ይቀጥላል፡፡ ኢትዮጵያ ሰኔ ወር ላይ ከሜዳዋ ውጭ ከቦትስዋና እና በሜዳዋ ከደቡብ አፍሪካ ጋር ትገናኛለች፡፡ በእነዚህ የ4ኛ እና የ5ኛ ዙር የማጣርያ ጨዋታዎች ካሸነፈች በ6ኛ ዙር ከሜዳዋ ውጭ ከመካከለኛው አፍሪካ የምታደርገውን የመጨረሻ ጨዋታ ሳትጠብቅ ምድብ አንድን በመሪነት በማጠናቀቅ ለመጨረሻው የጥሎ ማለፍ ማጣርያ ታልፋለች፡፡

በተያያዘ በ2013 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ አንደኛ ዙር ማጣርያ ተጋጣሚዎቻቸውን የረቱት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት የመልስ ጨዋታቸውን ከሳምንት በኋላ ያደርጋሉ፡፡ በአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ የአንደኛ ዙር ማጣርያ የመጀመርያ ግጥሚያውን በሜዳው ያደረገው ቅዱስ ጊዮርጊስ የማሊውን ዲጆሊባ 2-0 ማሸነፉ ሲታወስ፤ በኮንፌዴሬሽን ካፕ ደግሞ የአንደኛ ዙር የማጣርያ ጨዋታውን ከሜዳው ውጭ ወደ ሱዳን ተጉዞ አልሼንዲን የገጠመው ደደቢት 1-0 በሆነ ጠባብ ውጤት እንዳሸነፈ አይዘነጋም፡፡ የአንደኛ ዙር ማጣርያ የመልስ ጨዋታዎች ሲቀጥሉ ሁለቱ የኢትዮጵያ ክለቦች ወደ ሁለተኛ ዙር የማጣርያ ምእራፍ ለመሸጋገር የሚያስችል ዕድል ይዘዋል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሻምፒዮንስ ሊጉ ከሜዳው ውጭ በባማኮ የማሊውን ዲጆሊባ ሲፋለም ማሸነፍ እና አቻ መውጣት የሚበቃው ሲሆን ዲጆሊባ ጊዮርጊስን ጥሎ ለማለፍ በሜዳው የሚያደርገውን ግጥሚያ 3-0 ማሸነፍ ይኖርበታል፡፡ በሌላ በኩል በኮንፌደሬሽን ካፕ አዲስ አበባ ላይ የሱዳኑን አልሼንዲን የሚያስተናግደው ደደቢት በሜዳውና በደጋፊው ፊት በሚያደርገው የመልስ ጨዋታ በማሸነፍ የማለፍ እድሉን ይወስናል፡፡

በአውሮፓ 5 ታላላቅ ሊጎች የ2012 -13 የውድድር ዘመንን ሲጠናቀቅ ከሁለት ወር ያነሰ ጊዜ ሲቀረው በየሊጐቹ የሻምፒዮናነት ፉክክሩ ብዙም አጓጊ አይደለም፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ማን ዩናይትድ፤ በስፔን ላሊጋ ባርሴሎና እንዲሁም በጀርመን ቦንደስ ሊጋ ባየር ሙኒክ የየሊጋቸውን የደረጃ ሰንጠረዥ በሰፊ የነጥብ ልዩነት በመምራት ወደ ሻምፒዮናነቱ ያለ ተፎካካሪ እየገሰገሱ ናቸው፡፡ በጣሊያን ሴሪኤ እና በፈረንሳይ ሊግ 1 ግን የዋንጫ ፉክክሩ ብዙም አልደበዘዘም፡፡ በአውሮፓ 5 ታላላቅ ሊጎች ላይ ለዋንጫዎች የሚደረግ ፉክክር በጥቂት ክለቦች መካከል ተወስኖ የየሊጎቹን ማራኪነት እየቀዘቀዘው መጥቷል፡፡ ለዚህም ባለፉት 10 ዓመታት በአምስቱ የአውሮፓ ሊጎች በሚወዳደሩ ክለቦች መካከል በፋይናንስ አቅም የተፈጠረው ልዩነት ዋና ምክንያት መሆኑ ይገለፃል፡፡ የጀርመኑ ቦንደስ ሊጋ እና የፈረንሳዩ ሊግ 1 በሚታይባቸው የፉክክር ደረጃ እና የክለቦች የተመጣጠነ አቋም አጓጊ እና ውጤታቸውን ለመተንበይ የሚያስቸግሩ ሊጎች ናቸው፡፡ የስፔኑ ላሊጋ ደግሞ በሁለት ክለቦች ብቻ በተወሰነ ፉክክር ሚዛኑ ያጣ እና የማይስብ ሊግ ሲባል የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ትርፋማ የጣሊያን ሴሪኤ ደግሞ ደካማ ሊጐች ተብለዋል፡፡

በ21ኛው የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ እስከ 29ኛው ሳምንት በተደረጉ 296 ጨዋታዎች 837 ጎሎች ተመዝግበው ሊጉ በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.83 ጎሎች የሚቆጠሩበት ሆኗል፡፡ ማንችስተር ዩናይትድ ፕሪሚዬር ሊጉን ከ29 ጨዋታዎች በሰበሰባቸው 74 ነጥቦች እና 38 የግብ ክፍያዎች እየመራ ነው፡፡ ያለፈው ዓመት የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ማንችስተር ሲቲ በ59 ነጥብ እንዲሁም ቼልሲ በ55 ነጥብ ይከተላሉ፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን በመጨረሻ ሳምንት ጨዋታዎች እንደታወቀ ሲታወስ ዘንድሮ ግን ሊጉ ከመጠናቀቁ ወር ቀደም ብሎ አሸናፊው ይለያል፡፡ ሰር አሌክስ ፈርጉሰን ክለባቸው በፍፁም የበላይነት የዋንጫ ፉክክሩን መጨረሱ የሚዲያዎችን ትኩረት ቢቀንስም እንዳስደነቃቸው ተናግረዋል፡፡ የፕሪሚዬር ሊጉ የዋንጫ ፉክክር ቢቀዛቀዝም በቀጣይ የውድድር ዘመን የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፎ ለማግኘት በ7 ነጥብ ልዩነት አራት ክለቦች አስጨናቂ ፉክክር ውስጥ ናቸው፡፡ አራቱ ክለቦች ቼልሲ፤ ቶትንሃም፤ አርሰናልና ኤቨርተን ሲሆኑ በቂ ጨዋታዎቻቸው እስከ አራተኛ ደረጃ ለመጨረስ ወሳኝ ፍልሚያዎችን ያደርጋሉ፡፡

ቼልሲ እና ቶትንሃም በቀሪ ግጥሚያዎቻቸው ከባድ ተጋጣሚዎእች ያሉባቸው ሲሆን አርሰናልና ኤቨርተን ቀለል ባሉ ጨዋታዎች የሻምፒዮንስ ሊግ ተሳትፏቸውን ለማሳካት ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ኪውፒአር ሬዲንግ እና ዊጋን በወራጅ ቀጠና ውስጥ እየዳከሩ ሲሆን አስቶንቪላ፤ ሳውዝ ሃምፕተንና ሰንደርላንድ በዚሁ አደጋ አፋፍ ላይ ሆነው በቀጣዮቹ አምስት ሳምንታት ከመውረድ ለመዳን ይታገላሉ፡፡ በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የዓመቱ ኮከብ ተጨዋች ፉክክር የማን ዩናይትዱ ቫን ፒርሲ፤ የቶትንሃሙ ጋሬዝ ባሌ እና የሊቨርፑሉ ሊውስ ስዋሬዝ ዋና እጩዎእች ናቸው፡፡ የኮከብ ግብ አግቢነቱን ፉክክር ደግሞ የሊቨርፑሉ ሊውስ ሱዋሬዝ በ22 ጎሎች ሲመራ የማን ዩናይትዱ ቫንፒርሲ በ19 ጎሎች ዱካውን ይዞታል፡፡ በታሪኩ ለ82ኛ ጊዜ እየተካሄደ በሚገኘው የስፔኑ ላሊጋ እስከ 28ኛው ሳምንት 283 ጨዋታዎች ተደርገው 791 ጎሎች ከመረብ አርፈዋል፡፡

ይህም የላሊጋውን አንድ ጨዋታ በአማካይ 2.83 ጎሎች የሚመዘገቡበት አድርጎታል፡፡ በላሊጋው ባርሴሎና ባደረጋቸው 28 ግጥሚያዎች 74 ነጥብ እና 54 የግብ ክፍያ መሪነቱን እንደያዘ ሲሆን ያለፈው ሻምፒዮን ሪያል ማድሪድ በ13 ነጥብ ተበልጦ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ነው፡፡ በኮከብ ግብ አግቢ ፉክክር ደግሞ የባርሴሎናው ሊዮኔል ሜሲ በ42 ጎሎቹ የሚመራ ሲሆን የሪያል ማድሪዱ ክርስትያኖ ሮናልዶ በ27 ጎሎች በርቀት ይከተለዋል፡፡ በ50ኛው የጀርመን ቦንደስ ሊጋ እስከ 26ኛው ሳምንት በተደረጉ 234 ጨዋታዎች 665 ጎሎች ተመዝግበው ሊጉ በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.84 ጎሎች የሚያሳይ ሆኗል፡፡ ባየር ሙኒክ ባደረጋቸው 26 ጨዋታዎች 69 ነጥብ እና 58 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ቦንደስ ሊጋውን በሁለተኛ ደረጃ ከሚገኘው ቦርስያ ዶርትመንድ በ20 ነጥብ ልዩነት መሪነቱን ይዞ ወደ ሻምፒዮናነት እየገሰገሰ ነው፡፡ በኮከብ አግቢ ፉክክር የቦርስያ ዶርትመንዱ ሮበርት ሌዋንዶውስኪ በ19 ጎሎች እየመራ ሲሆን የባየር ሌቨርኩዘኑ ስቴፈን ኪዬብሊንግ በ16 ጎሎች እንዲሁም የባየር ሙኒኩ ማርዮ ማንዱዚክ በ15 ጎሎች ይከተሉታል፡፡

በ81ኛው የጣሊያን ሴሪ ኤ እስከ 29ኛው ሳምንት በተደረጉ 289 ጨዋታዎች 772 ጎሎች የገቡ ሲሆን ይህም በሴሪኤው በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.67 ጎሎች ሲቆጠሩ ቆይተዋል፡፡ ያለፈው አመት የሴሪኤ ሻምፒዮን ጁቬንትስ ዘንድሮም የስኩዴቶውን ክብር የመውሰድ እድሉን እያሰፋ ሲሆን ባደረጋቸው 29 ጨዋታዎች 65 ነጥብና 39 የግብ ክፍያ በመያዝ ይመራል፡፡ ናፖሊ በ56 ነጥብ እንዲሁም ኤሲ ሚላን በ54 ነጥብ እየተከተሉ ናቸው፡፡ በሴሪኤው የኮከብ ግብ አግቢነቱን ፉክክር የሚመራው የናፖሊው ኤዲሰን ካቫኒ በ20 ጎሎች ነው፡፡ በ75ኛው የፈረንሳይ ሊግ 1 እስከ 29ኛው ሳምንት በተደረጉ 290 ጨዋታዎች 735 ጎሎች ሲቆጠሩ ይህም ሊጉን በአንድ ጨዋታ በአማካይ 2.53 ጎሎች የሚገቡበት አድርጎታል፡፡ በሊግ 1 ባደረጋቸው 29 ጨዋታዎች 58 ነጥብ እና 33 የግብ ክፍያ በማስመዝገብ ፓሪስ ሴንትዠርመን እየመራ ቢሆንም ሊዮን በ53 እንዲሁም ማርሴይ በ51 ነጥብ በሁለተኛ እና ሶስትኛ ደረጃ እየተፎካከሩ ናቸው፡፡ በኮከብ ግብ አግቢነት ፉክክሩ የፓሪስ ሴንትዠርመኑ ዝላታን ኢብራሞቪች በ25 ጎሎች ይመራል፡፡

Saturday, 30 March 2013 14:44

የዝነኛው እጣፈንታ!

“ምንድነው ዝነኝነት ሰለቸኝ ብሎ ነገር? ከሙያህ ለመውጣት ሌላ አሳማኝ ምክንያት ካለህ ንገረኝና ልቀበልህ፡፡ ተራ ሰው ሆኖ መኖር አማረኝ ማለት ግን …” አለ መርዕድ የሰለሞን ነገር አልዋጥልህ ብሎት፡፡ ለሀያ አመት በዘለቀው የፕሮሞተርነት ስራው እንደዚህ አይነት እንግዳ ነገር ሰምቶ አያውቅም፡፡ አንድ ድምፃዊ ዝነኝነት ሰለቸኝ ብሎ ድምፃዊነቱን እርግፍ አድርጎ ለመተው ሲወስን የአሁኑ የመጀመርያው ነው፡፡ ለዛውም እንደ ሰለሞን ያለ ባወጣቸው ስድስት የዘፈን አልበሞቹ በሙሉ የተሳካለት፤ በየትኛውም ስፍራ ያሉ አድናቂዎቹ ሥራውን ካላቀረበልን እያሉ በየሚዲያው የሚወተወቱት አርቲስት እንዴት ዝነኝነት ሰለቸኝ ይላል? “ሌላ ምክንያት የለኝም! … ዝነኛ ሆኖ መኖር ሰልችቶኛል፡፡ ዝነኝነትን መጥላቴ ሙያዬን እንድተው እንዳስገደደኝ ስነግርህ ማመን ካቃተህ ምን አደርጋለሁ? በቃ ተራ ሰው የሚኖረው ኑሮ አማረኝ፡፡” ዝነኛው ድምፃዊ ሰለሞን እረጋ ብሎ ነው የሚያወራው፡፡ ፕሮሞተሩ መርዕድ ቢቀበለውም ባይቀበለውም ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ የዝነኝነት ከፍታ ላይ ካወጣው ሙያው ለመለያየት ቁርጥ ውሳኔ ላይ ደርሷል፡፡

“እኮ አስረዳኝ! … ስንቶች ዝነኛ ለመሆን እንቅልፍ አጥተው ሲፍጨረጨሩ … አንተ ግን ዝነኝነት ሰለቸኝ ብለህ… ፈፅሞ ልትገባኝ አልቻልክም፡፡ ቆይ ዝነኝነት እንዴት ይሰለቻል? ዝነኛ ስትሆን እኮ ሰው ያከብርሀል፣ ሰላም ይልሀል፣ ቅድሚያ ይሰጥሀል” …ላንተ ምን እነግርሃለሁ መርዕድ በሃፍረት ስሜት ሰለሞን ላይ አፈጠጠ፡፡ ሰለሞን ከሙዚቃው ዓለም ሲወጣ በፕሮሞተርነቱ ብዙ ነገር እንደሚያጎልበት ይውቃል፡፡ ከግሉ ጉዳት በላይ ደግም በሀገሪቷ ሙዚቃ እድገት ላይ የሚኖረው ተፅዕኖ ቀላል እንደማይሆን ያውቃል፡፡ ሰለሞን ተራ ድምፃዊ አይደለም፤ ኃላፊነት የሚሰማው ለብዙዎች አርአያ መሆን የሚችል በሳል አርቲስትም ጭምር ነው፡፡

“ዝነኝነት ይሰለቻል! እ…ዝነኝነት ማለት በተራራ ላይ መስታወት ቤት ውስጥ እንደመኖር ነው፡፡ ሁሉም ያይሃል፣ ሁሉም ይከታተልሃል … ለብቻህ በነፃነት የምታደርገው ነገር የሌለህ ፍጡር ነህ! ነፃነት አልባ ፍጡር!” ሰለሞን ዝነኝነትን በመንገሽገሽ ንግግሩን ቀጠለ፡፡ “የመጀመሪያ ካሴቴን ከማውጣቴ በፊት የነበረኝን ነፃነት ሳስበው እገረማለሁ፡፡ ስፈልግ በመንገድ ላይ እጆቼን ኪሶቼ ውስጥ ከትቼ፣ አሊያም ግስላ ሲጃራዬን እያጨስኩ፣ ከሰዎች ጋር እየተጋፋሁ፣ ህብረተሰቡ የሚያወራውንና የሚያማውን እየሰማሁ … መሔድ፤ መኖር ብዙ ትርጉም እንዳለው የገባኝ ዝነኛ ከሆንኩ በኋላ ነው - አሁን!…” ሰለሞን ለአፍታ ትንፋሽ ወሰደና በስሜት መናገሩን ገፋበት፤ “አሁን ዝነኛ ከሆንኩ በኋላስ? ሽንቴን መንገድ ላይ ቢወጥረኝ እንኳ ፊኛዬ ይፈነዳታል እንጂ መንገድ ላይ እንኳ ቆሜ መሽናት አልችልም! … መንገዱ ቀርቶ የህዝብ ሽንት ቤት መግባት እንኳ አልችልም፡፡

የፈለግኋትን ቆንጆ መንገድ ላይ ተከትዬ የመጥበስ እንኳን ነፃነት የለኝም እኮ! ይኼ ሁሉ በዝነኝነቴ የመጣ ባርነት ነው!” “እነዚህ ሁሉ ትርጉም የሌላቸው! ተራ ነገሮች እኮ ናቸው!” አለ መርዕድ በማቃለል “ትርጉምማ አላቸው! ነገሩን አልኩህ እንጂ እነዚህን ነገሮች ማድረግ ትክክል ነው ማለቴ አይደለም፡፡ መንገድ ላይ የማልሸናው ዝነኛ ስለሆንኩ ነው እንጂ መንገድ ላይ መሽናት ትክክል እንዳልሆነ ስላመንኩ አይደለም!” ከመርዕድ ምላሽ የፈለገ አይመስልም፡፡ “እነዚህ ሁሉ ተራ ነገሮች የነፃነት ምልክቶች ናቸው፡፡ ሰው ነፃነት ለማግኘት ጠመንጃ ያነሳል እኮ መርዕድ! የነፃነት ግንባር ብሎ ሰይሞ ድርጅት እስከማቋቋም ይደርሳል እኮ … አስበው ሰዎች ህይወታቸውን የሚገብሩለትን ነፃነት በዝነኝነት ሰበብ ስታጣው፡፡ መንገድ ላይ ቆሞ መሽናት እንኳን ብርቅ ይሆንብሀል እኮ፣ መንገድ ላይ የተጠበሰ በቆሎ እየበላህ መሔድ እንኳን አትችልም፡፡ ለምን? ዝነኛ ነሃ!” ሰለሞን ሀሳቡን በቅጡ የሚገልጡለት ቃላት ያገኘ አልመሰለውም፡፡ “ያልከው ባይገባኝም እስቲ ሙያህን አቆምክ ብለን እንውሰድ፡፡ ከዛስ ዝነኝነትህን እንደ አረጀ ኮት አጣጥፈህ ማስቀመጥ የምትችል ይመስልሀል? ሸሽተኸው ማምለጥ እንዳትችል በስድስት አልበሞች የሰራሃቸው ስራዎች ይከተሉሀል፡፡ በስድስት አልበሞች የተገነባ ዝነኝነትን እንደቀልድ ከላይህ ላይ አራግፈህ ልትጥለው… አይሆንማ! … መርዕድ ከተቀመጠበት ወንበር ላይ በስሜት እየተውረገረገ ተነሳ፡፡ “አይምሰልህ ዝነኝነት እንደ አበባ ነው… ሰርክ እየኮተኮትክ፣ ውሀ እያጠጣህ የምትንከባከበው፡፡ አበባን ካልተንከባከብከው እየቆየ እንደሚከስመው ዝነኝነትም በጊዜ ሒደት ቀለሙ እየጠፋ ይኼዳል፡፡

እከሌ እኮ ድሮ የታወቀ አርቲስት ነበር ብትል ታሪክ ነው የሚሆነው፡፡ ልክ ታዋቂ አትሌት ነበር እንደምትለው … ቢበዛ ከንፈር የሚመጥልህ ሰው ብታገኝ ነው እንጂ መውጫ መግቢያ የሚያሳጣህ ሰው አይኖርም” አለ ሰለሞን፡፡ “እና ታሪክ ለመሆን አቅጃለሁ ነው የምትለኝ?” መርዕድ በጥርጣሬ መንፈስ ተሞልቶ ጠየቀው፡፡ ሰለሞን በአዎንታ እራሱን ነቀነቀ፡፡ “አዎ! እኔ የማንም አርአያ የመሆን ፍላጎት የለኝም፡፡ ዝነኝነቴን ወስዳችሁ ነፃነቴን መልሱልኝ እያልኩ ነው!” አለ ሰለሞን ከተቀመጠበት እየተነሳ፡፡ መርዕድ ምንም ሊያደርግ እንደማይችል ተረድቶታል፡፡ ተስፋ በቆረጠ ስሜት ለስንብት እጁን ዘረጋለትና ተጨባበጡ፡፡ “ዝነኝነት ሱስ ነው፡፡ ወይም ደግሞ ልክፍት! እርግጠኛ ነኝ በድጋሚ ዝነኝነት ይናፍቅሃል! ተራ ሰው ሆነህ ሀምሳ አመት ከመኖር ዝነኛ ሆነህ ሀምሳ ቀን መኖር እንደምትመርጥ አልጠራጠርም! … ያን ጊዜ በሬ ክፍት ነው፡፡ እስከዛው ግን ቢያንስ የት እንደምትሔድ ንገረኝ እና እየመጣሁ ልጠይቅህ፡፡” አለ መርዕድ ሰለሞን በአሉታ እራሱን ግራና ቀኝ ወዘወዘ “ይቅርታ መርዕድ፤ ዝነኝነት ለኔ ቀንበር ነው እንጂ ሀብል አይደለም፡፡ ወደ ዝነኝነቴ የሚመልሱኝን ድልድዮች ሰብሬ መሔድ ነው የምፈልገው፡፡ አንዳንዶች ዝነኛ ሆነው ለመኖር ብርቱ ጫንቃ አላቸው፤ እኔ ግን ፈፅሞ የለኝም! ዝነኝነትን መቋቋም የሚችል ትከሻ አልተሰጠኝም!” አለና ተንደርድሮ ከመርዕድ ቢሮ ወጣ፡፡ የውጪው ነፋሻ አየር ተቀበለው፡፡ ጀንበር ወደመጥለቂያዋ እያቆለቆለች ስለነበር ወርቅማ የስንብት ቀለሟን እሱን ወክላ የምትረጭ መሰለው፡፡ ጀንበሯን ተከትሎ “ዝነኝነት ያላጎበጠው ነፃ ሰው! ዝነኝነት ያልከበበው ነፃ ማንነት!” እያለ መጮህ ናፈቀው፡፡

ጀንበሯን ቆሞ በሰመመን ሲቃኝ ከጀርባው አንድ ድምፅ ሰማ፤ “እንዴ ሰለሞን! ታዋቂው ድምፃዊ ሰለሞን! ሰሌ! ሰሌ!!!” የሚል ጩኸት ሙሉ በሙሉ ከሰመመኑ አነቃው፡፡ ህፃናት፣ ኮረዶች፣ ጎልማሶች … የአካባቢው ሰዎች ሁሉ ከየቤታቸው ወጥተው እንደ ጉንዳን እየከበቡት መሆኑን ሲረዳ መኪናውን ያቆመበትን ቦታ ተመለከተ - ለማምለጥ! “ሰሌ! ፍቅር እና ትዝታ የሚለው ዘፈንህ ተመችቶኛል!...”፣ ሰሌ! “እዚች ጋር ትፈርምልኛለህ?” “ሰሌ! እንወድሃለን!” የሚሉና ሌሎች ድምፆች ከበቡት፡፡ ጨነቀው፡፡ ለከበበው ህዝብ “እኔ ዘፋኙ ሰለሞን አይደለሁም!” ብሎ ለመጮህ፤ ለማወጅ አስቦ ነበር፡፡ ግን አይገባቸውም በሚል ተወው፡፡ ከላይ እየበረረች የምትመጣ ላዳ ታክሲ ሲያይ አስቁሞ ዘሎ ገባ፡፡ የታክሲው ሾፌር በኋላ ማሳያ መስታወቱ አየውና ፈገግ አለ፡፡ “ምነው ቢኤም ደብሊዋ ደበረችህ እንዴ?” ጠየቀው ሾፌሩ፡፡ “መኪናዬ ቢኤም ደብሊው መሆኗን እንኳ ይኼ ሾፌር ያውቃል! የኔ ብቻ የምለው ምስጢር የሌለኝ ምስኪን ሰው!” እያለ በውስጡ በምሬት ይብሰለሰል ገባ፡፡

አፉ ላይ የመጣለትን መናኛ መልስ ለሾፌሩ ሰጠውና ወደ ራሱ ሀሳብ ተመለሰ፡፡ “ዝነኝነት ታዲያ ምኑ ነው የሚያስደስተው? ሰዎች በታክሲ መሳፈር እንዳለብህ እና እንደሌለብህ ይወስኑልሀል! የምትመገብበትን ምግብ ቤት የሚወስኑልህ ሌሎች ናቸው! ነፃነት የሌለው ህይወት ሲኦል አይደለም እንዴ?!” ከራሱ ጋር እያወራና ብቻውን እየተብከነከነ ሳለ ባለታክሲው አሁንም ሳቅ ብሎ ተመለከተውና “አልጋ የያዝክበት ሆቴል ደርሰናል!” አለው፡፡ “እዚህ አልጋ እንደያዝኩ በምን አወቀ?” ንዴት በሰራ አካላቱ ተቀጣጠለ፡፡ ባለታክሲውን በንዴት ገረመመውና እጁ ላይ የገባለትን ብር ከቦርሳው መዥረጥ አድርጎ ወርውሮለት ከታክሲው ውስጥ ዘሎ ወጣ፡፡ የነፃነት እጦት ትንፋሽ ያሳጣው መሰለው፡፡ እየሮጠ ወደ ያዘው የመኝታ ክፍል ሮጠ፡፡ ፍቅረኛው ካትሪን አልጋ ላይ ጋደም ብላ መፅሀፍ ታነባለች፡፡ ካትሪን የስዊዲን ተወላጅ ናት፡፡ ከሰለሞን ጋር ድንገት ነበር በግብዣ ላይ የተዋወቁት፡፡

ያኔ ካትሪን ስለሰለሞን ዝነኝነት ምንም የምታውቀው ነገር አልነበራትም፡፡ ለዚህ ነው ከመቅፅበት በፍቅር የወደቀላት፡፡ ሰው በመሆኑ ብቻ የምትቀርበው እንስት ሲፈልግ ነው ያገኛት፡፡ ከሀገሩ እንስቶች ሊያገኝ ያልቻለው ይህንን አይነቱን ፍቅር ነበር፡፡ ሁሉም ሴቶች እሱን ከማወቃቸው በፊት ከዝነኝነቱ ጋር በፍቅር እየወደቁ በተቸገረበት ወቅት ካትሪን ባህር ተሻግራ ደረሰችለት፡፡ የሀገሩ ሴቶች “ወይኔ ሰሌ! የመጨረሻው ካሴትህ ላይ ያለውን ‘ፍቅር ይዞኝ ነበር’ የሚል ዜማ እንዴት እንደወደድኩት!” ሲሉት የፍቅር ተስፋው እንደጉም ይበናል፡፡ የካተሪን ግን የተለየ ነበር፡፡ መጀመሪያ ሰለሞንነቱን ነው የወደደችው… ወደ ክፍሉ እየሮጠ ሲገባ ካትሪን ደንግጣ ከአልጋዋ ተነሳች፡፡

“ከማበዴ በፊት አሁኑኑ ይኼን ከተማ ለቅቄ መሄድ አለብኝ!” አላት ሰለሞን፡፡ ሁኔታው ግራ ስላጋባት ምንም ነገር ልትጠይቀው አልደፈረችም፡፡ ልብሷን ቀያይራ ተከተለችው፡፡ እስከ ሀዋሳ ድረስም ሸኘችው፡፡ የሰለሞን ጉዞ ግን እዛ የሚያቆም አልነበረም፡፡ ከተማን ነበር ሽሽቱ… ቴሌቭዥን ብሎ ነገር የሌለበት፣ ኢንተርኔት ይሉት ጉድ ያልገባበት፣ ተፈጥሮ እና ተፈጥሮ ብቻ ወዳሉበት ምድር መሄድ… ለዚህ ደግሞ ከደቡብ ኢትዮጵያ የተሻለ… ከፀማይ መንደር የበለጠ አማራጭ አልነበረውም፡፡ ፀማይ ዝነኝነቱን እንድታከሰምለት የመረጣት ምድር ሆነች፡፡ በተፈጥሮዋ ጭምቅ አድርጋ ዝነኝነት የሚባለውን አውሬ ሲጥ እንደምታደርግለት ተማምኖባታል፡፡

*** ከሁለት ወር በኋላ… ሰው መሆን ብቻ በቂ የሆነባት ምድር-ፀማይ! ማነህ? ምንድነህ? የሚል ጥያቄ የሌለባት፣ የሰው ልጅ ከቁስ አካላዊ ግብዝነቱ ተላቆ ሲኖር ምን ያህል ውብ እንደሆነ የሚታይባት ምድር! ሰርክ ጠዋት ከእንቅልፉ ሲነቃ በህልም አለም እንደሚኖር ነው የሚሰማው፡፡ የስልክ ጥሪ ሳይሆን የከብቶች እንቧታ ከእንቅልፉ ሲቀሰቅሰው ደስታው ወሰን ያጣል፡፡ ፀማይ ውስጥ የፈርምልኝ ጫጫታ አያጋጥመውም! “አርቲስት ሰለሞን በኩረ፤ ሶደሬ አካባቢ በተደጋጋሚ ይታያል”፣ “አርቲስት ሰለሞን በኩረ፤ ከአዲሷ ፍቅረኛው ጋር በተደጋጋሚ ፀብ ውስጥ እየገባ ነው”፣ “አርቲስት ሰለሞን በኩረ፤ ጫማውን ለጠረገለት ሊስትሮ ሁለት መቶ ብር ሰጠ”፣ “አርቲስት ሰለሞን በኩረ፤ በተደጋጋሚ ሽሮ መብላቱ ለድምፁ አስተዋፅኦ ይኖረው ይሆን?”... ቅብርጥሶ ምንትሶ ከሚሉ የጋዜጣ እና መፅሄት አናዳጅ ዘገባዎች ተገላግሏል፡፡ አናዳጅ የጋዜጠኛ ጥያቄዎችም ፀማይ ውስጥ የሉም! “አርቲስት ሰለሞን፤ በልጅነትህ መጫወት የምትወደው ጨዋታ ምን ነበር?” (እርግጫ ቢላቸው ይወዳል ግን ዋና እወዳለሁ ይላል) የህይወት ፍልስፍናህ ምን ነበር?” (እኔ እኮ ዘፋኝ እንጂ ፈላስፋ አይደለሁም ቢላቸው ይወዳል፤ ግን ከሰው ጋር አብሮ መኖር ምናምን የሚል ፍልስፍና አለኝ ይላቸዋል) “አርቲስት ሰለሞን፤ ወደፊት ምን ለመሆን ትፈልጋለህ?” (ጋዜጠኛውን እያየ የአንተን አይነሰብ በቡጢ መነረት ማለት ይፈልጋል፤ ግን በሙያዬ ትልቅ ደረጃ ላይ መድረስ ይላቸዋል)፡፡ አሁን እነዚህ ጥያቄዎች ምን ይሰራሉ? ስለዘፈኑ ሙያዊ ጥያቄ የጠየቀው አንድም ጋዜጠኛ አያስታውስም፡፡ በቀን ለስንት ሰአት ትተኛለህ? ምግብ ማብሰል ደስ ይልሃል? የመጀመሪያ ፍቅረኛህን የት ተዋወቅሃት?... ሁሉም ስለሱ ነው ማወቅ የሚፈልጉት! የራሴ የሚለው ነገር እንዲኖረው አይፈልጉም፡፡

የማስመሰል ህይወት ፀማይ ውስጥ የለም! በጫት እና በሺሻ ታጥረው እየዋሉ “እኛ አርቲስቶች ከሱስ የፀዳ ህብረተሰብ ለመፍጠር አርአያ መሆን አለብን!” የሚል ዲስኩር ማሰማት በፀማይ ውስጥ የለም፡፡ ጠዋት ስለጫት አስከፊነት አውርቶ ከሰአት “ልጄ የጥበብ ሥራ በርጫ ይዘው በፅሞና ነው! ሼክስፒር ሳይቅም እንዲህ የፃፈ ቢቅም ኖሮ የትናየት በደረሰ ነበር!…” ማለት የለም፡፡ ህዝቡን መድረክ ላይ አስር ጊዜ “በጣም ነው የምወዳችሁ!” እያሉ በመወሻከት የቁርጥ ቀን ሲመጣ “ልጄ ሁሉም ለራሱ ነው!” ብሎ ነገር የለም፡፡ ፀማይ የእውነት ምድር ነው፡፡ መውደድ እንዳይረክስ በቃል አይጠራም፤ በተግባር ነው የሚገለፀው፡፡ እነዚህን ሁሉ በረከቶች አግኝቷል፡፡ ፀማይ ሰላም ነው! በፀማይ ኮረብቶች፣ በፀማይ ሜዳዎች ላይ ቀን ከምሽት ሳይመርጥ ሲንጐራደድ፣ አፉ ውስጥ የቀረች አንዲት ግጥምን እንደ ብሔራዊ መዝሙር ይደጋግማታል፡፡

“ፍላጐት ምኞትህ ወደብ ድንበር አለው? ብለህ አትጠይቀኝ ህልሜ አንተን መሆን ነው! ያለ ስም ቅጥያ ግቤ ሰው መሆን ነው፡፡ ሰው መሆን! ሰው መሆን! በቃ ነፃ መሆን!” ግጥሟ የአንድ ፋርሳዊ ፀሃፊ ነው ብሎ ጓደኛው ነበር በቃሉ ያስጠናው፡፡ ነፃ ሰው የመሆን ስሜቱን በፀማይ አፈር፣ በፀማይ አየር፣ በፀማይ ሰዎች መካከል አግኝቶታል፡፡ ከሁሉ በላይ ደግሞ ከኦሞ ወንዝ ጋር የማይደበዝዝ ፍቅር አዳብሮ ነበር፡፡ ኦሞን እንደሰው እያዋራ፣ በኦሞ የቅዝቃዜ በረከት ሲረሰርስ፣ በኦሞ ፈሳሽ ውሃ ሲዳሰስ ዘላለማዊ መኖሪያው በኦሞ ዳርቻ እንደሚሆን ወስኖ ነበር፡፡ በሰለሞን ውሳኔ ግን ኦሞ የተስማማ አይመስልም፡፡ እጣውን ኦሞ እራሱ ፅፎ ሰጠው፡፡ እጣ ደግሞ የሚመርጡት ሳይሆን የሚወጣ ነው፡፡ በአንድ ወበቃማ ቀን ሰለሞን ወደ ኦሞ ሲወርድ ለሁለት ወራት ያህል ከውሀው ሲገባ ለወትሮ የሚያገኘውን ደስታ በልቡ እያሰበ ነበር፡፡ ወደ ወንዙ የሚያመራውን ጉብታ ቁልቁል እያቋረጠ ሳለ ግን የድረሱልኝ የሚመስል ድምፅ የሰማ መሰለው፡፡ እየሮጠ ወደ ወንዙ ደረሰ፡፡

ብቅ ጥልቅ የሚል ሰው ታየው፡፡ በውሀው ላለመወሰድ የሚታገል፡፡ ዘሎ ከውሀው ገባ፡፡ የውሃውን ሃይል እየታገለ ሰው ወዳየበት አቅጣጫ ተምዘገዘገ፡፡ ያየውን ሰው እጅ እንዳገኘ ሽቅብ ገፋው እና ከውሀው በላይ አደረገው፡፡ በአንድ እጁ እየዋኘ ወደ ወንዙ ዳር ተጠጋ፡፡ ኦሞ እንደለማዳ ፈረስ እሺ ብሎ የሚጋልብለት ይመስል በቀላሉ አቋረጠው፡፡ የተሸከመውን ሰው አውጥቶ ከወንዙ ዳር አስተኛው፡፡ በውሀ ሊወሰድ የነበረው ሰው ግዙፍ ወንድ ነበር - ፈረንጅ! ከአለባበሱ ቱሪስት እንደሆነ ገምቷል፡፡ ከነልብሱ ምን ሊያደርግ ኦሞ ውስጥ እንደገባ ለሰለሞን ሊገባው አልቻለም፡፡ “እንደኔ የከተማ ቱማታ ናላውን ያዞረው ይሆናል!” ብሎ እያሰበ ሳለ፣ የፈረንጁን ጩኸት የሰሙ ፀማዮች እየተጠራሩ ከቦታው ደረሱ፡፡ የሰውዬውን ደረት እየተጫኑ ከሆዱ የገባውን ውሀ ሲያስወጡለት ቀስ በቀስ ነፍስ ዘራ፡፡ ሰለሞን የሰው ነፍስ ማትረፍ መቻሉ ከፍተኛ ደስታ አጐናፅፎት ነበር፡፡ የፀማዮች ተደጋጋሚ የምስጋና ቃል ሲቸረው በሙሉ ልብ ሲቀበል ቆየ፡፡ ያረፈባት ቤት ፈረንጁን ከውሀ ውስጥ መንጥቆ ያወጣውን ጀግና ለማየት ከአቅራቢያ መንደሮች ጭምር በሚመጡ እንግዶች እስከምሽት ድረስ ተጨናነቀች፡፡ የሰለሞን ዝና በአንድ ምሽት ፀማይን አልፎ ጅንካ ደረሰ፡፡ ከጅንካ ምድር አልፎ አዋሳ ለመድረስ አንድ ቀን አልፈጀበትም፡፡ ከአዋሳ አዲስ አበባ በዚያው ቀን ምሽት ዜናው ተሰራጨ፡፡ የጋዜጠኞች ቡድን ካሜራ እና ማይኩን ደቅኖ ጀርመናዊውን ቱሪስት ያዳነውን ጀግና ለማየት ወደ ፀማይ አመራ፡፡

ሰለሞን ከከተማ የመጡ ሰዎች ሊያናግሩት እንደሚፈልጉ በብሔረሰቡ አባት ሲነገረው፤ ብዙም ደስ ባይለውም እሳቸውን ላለማስቀየም ወጥቶ የመጡትን ሰዎች ማነጋገር ነበረበት፡፡ “ለመንደራችን ልዩ ሲሳይ ነው ይዘህ የመጣኸው!... አሁንም ከከተማ ትላልቅ ሰዎች አንተን ለማነጋገር መጥተዋል፡፡ እንደምታየው መንደራችን ብዙም አላደገችም፡፡ አንተ የሰራኸው ስራ መንደራችንን ለማስተዋወቅ ጠቃሚ ነው!” የሚለው ንግግራቸው ይበልጥ አሳማኝ ሆነለት፡፡ ጋዜጠኞቹ ሰለሞንን ሲያዩ አይናቸውን ተጠራጥረው ነበር፡፡ ከመካከላቸው አንዱ፤ “ዝነኛው አርቲስት ሰለሞን?” አለ ባለማመን ስሜት ተውጦ ሰለሞን በአዎንታ እራሱን ነቀነቀ፡፡ የፎቶ ካሜራዎች ብልጭታ ከየቦታው ሲተኮስበት፣ የካሜራዎች እይታ እሱ ላይ ሲያነጣጥርበት አንድ ነገር ገባው፡፡ ዝነኝነት ምርጫው ባይሆንም እጣው ነበረ፡፡ ቢሸሽ የማያመልጠው! እንደ ጥላ!