Administrator

Administrator

ከዚህ ቀደም ለህዝብ ባቀረበቻቸውና ከፍተኛ ተወዳጅነት ባገኘችባቸው ”ላሊበላ“ ፣ ”ገዳም“ ፣ ”በላልበልሃ“ በተሰኙ ነጠላ ዜማዎቿ  የምትታወቀው ድምጻዊት ለምለም ኃ/ሚካኤል፤ ”ማያዬ“ የተሰኘ አዲስ የሙዚቃ አልበሟን የፊታችን አርብ ትለቃለች፡፡

ሰርቶ ለማጠናቀቅ ዘጠኝ ዓመት እንደፈጀ የተነገረለት አዲሱ የሙዚቃ አልበም 12 ያህል ዜማዎች የተካተቱበት ሲሆን፤ አንጋፋው ናሆም ሪከርድስ ፕሮዱዩስ አድርጎታል፡፡

በዚህ የሙዚቃ አልበም ውስጥ ኤልያስ መልካን ጨምሮ አንጋፋና ወጣት የሙዚቃ ባለሙያዎች ተሳትፈውበታል ተብሏል፡፡

አዲሱን የሙዚቃ አልበም  አስመልክቶ ዛሬ ግንቦት 3 ቀን 2016 ዓ.ም ረፋዱ ላይ ድምጻዊቷና የሙዚቃ ባለሙያዎች በማርዮት ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንደተነገረው፤ አበጋዝ ክብረወርቅ፣ ኤልያስ መልካ፣ ሚካኤል ሃይሉ፣ ታምሩ አማረ፣ አዲስ ፍቃዱና ብሩክ ተቀባ በቅንብር፤ ወንድወሰን ይሁብ፣ ናትናኤል ግርማቸው፣ ሀብታሙ ቦጋለ፣ ጥላሁን ሰማው፣ በግጥም ሲሳተፉ፤ ኤልያስ መልካ፣ አንተነህ ወራሽ፣ እሱባለው ይታየው፣ ብስራት ሱራፌል፣ ዘርአ ብሩክ ሰማው በዜማ ተሳትፈዋል፡፡ በሚክሲንግና ማስተሪንግ ሰለሞን ኃይለማርያም የተሳተፈ ሲሆን፤ በፕሮዱዩሰርነት ወንድወሰን ይሁብ እንደተሳተፈበት ታውቋል፡፡

”ማያዬ“ የተሰኘው የድምጻዊት ለምለም ኃ/ሚካኤል አዲስ የሙዚቃ አልበም የፊታችን አርብ ግንቦት 9 ቀን 2016 ዓ.ም በናሆም ሪኮርድስ የዩቲዩብ ቻናል እንዲሁም በዓለማቀፍ የሙዚቃ መተግበሪያዎች ይለቀቃል ተብሏል፡፡

በኦሮሚያ ክልል በባሌ አጋርፋ የተወለደችው ድምጻዊቷ፤ የሁለት ሴት ልጆች እናት ስትሆን፣ ላለፉት 10 ዓመታት በትወናና በድምጻዊነት የኪነጥበብ ዘርፍ ስታገለግል መቆየቷ ተጠቁሟል፡፡

ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በቲያትር ጥበባት ትምህርት የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘችው ለምለም ኃ/ሚካኤል፤ ከዚሁ የትምህርት ክፍል በቲያትር ፎር ዴቨሎፕመንት የሁለተኛ ድግሪ እጩ ተመራቂ ናት፡፡
የለምለም ኃ/ሚካኤል “ማያዬ” አዲስ የሙዚቃ አልበም የፊታችን አርብ ይለቀቃል  

ከዚህ ቀደም ለህዝብ ባቀረበቻቸውና ከፍተኛ ተወዳጅነት ባገኘችባቸው ”ላሊበላ“ ፣ ”ገዳም“ ፣ ”በላልበልሃ“ በተሰኙ ነጠላ ዜማዎቿ  የምትታወቀው ድምጻዊት ለምለም ኃ/ሚካኤል፤ ”ማያዬ“ የተሰኘ አዲስ የሙዚቃ አልበሟን የፊታችን አርብ ትለቃለች፡፡

ሰርቶ ለማጠናቀቅ ዘጠኝ ዓመት እንደፈጀ የተነገረለት አዲሱ የሙዚቃ አልበም 12 ያህል ዜማዎች የተካተቱበት ሲሆን፤ አንጋፋው ናሆም ሪከርድስ ፕሮዱዩስ አድርጎታል፡፡

በዚህ የሙዚቃ አልበም ውስጥ ኤልያስ መልካን ጨምሮ አንጋፋና ወጣት የሙዚቃ ባለሙያዎች ተሳትፈውበታል ተብሏል፡፡

አዲሱን የሙዚቃ አልበም  አስመልክቶ ዛሬ ግንቦት 3 ቀን 2016 ዓ.ም ረፋዱ ላይ ድምጻዊቷና የሙዚቃ ባለሙያዎች በማርዮት ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንደተነገረው፤ አበጋዝ ክብረወርቅ፣ ኤልያስ መልካ፣ ሚካኤል ሃይሉ፣ ታምሩ አማረ፣ አዲስ ፍቃዱና ብሩክ ተቀባ በቅንብር፤ ወንድወሰን ይሁብ፣ ናትናኤል ግርማቸው፣ ሀብታሙ ቦጋለ፣ ጥላሁን ሰማው፣ በግጥም ሲሳተፉ፤ ኤልያስ መልካ፣ አንተነህ ወራሽ፣ እሱባለው ይታየው፣ ብስራት ሱራፌል፣ ዘርአ ብሩክ ሰማው በዜማ ተሳትፈዋል፡፡ በሚክሲንግና ማስተሪንግ ሰለሞን ኃይለማርያም የተሳተፈ ሲሆን፤ በፕሮዱዩሰርነት ወንድወሰን ይሁብ እንደተሳተፈበት ታውቋል፡፡

”ማያዬ“ የተሰኘው የድምጻዊት ለምለም ኃ/ሚካኤል አዲስ የሙዚቃ አልበም የፊታችን አርብ ግንቦት 9 ቀን 2016 ዓ.ም በናሆም ሪኮርድስ የዩቲዩብ ቻናል እንዲሁም በዓለማቀፍ የሙዚቃ መተግበሪያዎች ይለቀቃል ተብሏል፡፡

በኦሮሚያ ክልል በባሌ አጋርፋ የተወለደችው ድምጻዊቷ፤ የሁለት ሴት ልጆች እናት ስትሆን፣ ላለፉት 10 ዓመታት በትወናና በድምጻዊነት የኪነጥበብ ዘርፍ ስታገለግል መቆየቷ ተጠቁሟል፡፡

ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በቲያትር ጥበባት ትምህርት የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘችው ለምለም ኃ/ሚካኤል፤ ከዚሁ የትምህርት ክፍል በቲያትር ፎር ዴቨሎፕመንት የሁለተኛ ድግሪ እጩ ተመራቂ ናት፡፡

Saturday, 11 May 2024 00:00

የተሻለ ይገባታል

    ለአንዲት ሀገር ሁለንተናዊና የተሟላ እድገት አስተማማኝነት፣ የስርአተ ጾታ እኩልነትን ማስፈንና በተለይም የህብረተሰብና የሀገር ተፈጥሮአዊ የህልውና መሰረት የሆኑትን ሴቶች ኢኮኖሚያዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት በማያወላዳ መልኩ ማረጋገጥ ለጥያቄ የማይቀርብ ቁልፍ ጉዳይ ነው፡፡
በከተማችን ባለፉት ተከታታይ የለውጥ አመታት ለትውልድ የሚተላለፉ ትላልቅና ግዙፍ ፕሮጀክቶችን በአጭር ጊዜ በመጨረስና ለህዝብ የገባውን ቃል በተግባር በማሳየት አንጸባራቂ ውጤቶችን ያስመዘገበው መንግስትም፤ የሴቶችን ጾታዊ ጥቃት ለመከላከልና ሁለንተናዊ ተሳትፎዋቸውንና ተጠቃሚነታቸውን ለማረጋገጥ የህግ ማዕቀፎችን ከማዘጋጀት ባለፈ አስተማማኝነቱ ሊረጋገጥ የሚችለው የተጋላጭነታቸውን ምንጭ በማድረቅና አስፈላጊውን ስራዎች በመስራት ላይ መሆኑን በተግባር ለማሳየት ቆርጦ በመነሳት፣ በከተማችን አዲስ አበባ ደቡባዊ አቅጣጫ፣ አቃቂ ቃሊቲ ክፍለከተማ በሀገራችን በአይነቱ የመጀመሪያው ፈርቀዳጅ የሆነ የሴቶች የተሀድሶና የክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከል በከፍተኛ ጥራት ገንብቶ በማጠናቀቅ ሌላኛውን ታሪካዊ አሻራ አኑሯል፡፡


ይህ ማእከል በአንድ ዙር በሺዎች የሚቆጠሩ የጾታዊ ጥቃት ሰለባ የሆኑ እና ለማህበራዊ ቀውስ የተጋለጡ ሴቶችን ያለአንዳች ቅድመ ሁኔታ ተቀብሎ ምግብ፤ መኝታና አልባሳትን ጨምሮ ሌሎች ሁሉን አቀፍ መሰረታዊ ፍላጎቶችን አቅርቦ ከሶስት እስከ ስድስት ወራት የሚቆይ ሞያዊና ስነ-ልቦናዊ ድጋፍና ስልጠናዎችን በመስጠት ስርነቀል ለውጥ ለማምጣት ጉልህ አስተዋጽኦ አለው፡፡ ማእከሉ በውስጡ ከሚሰጣቸው አገልግሎቶች መካከል የስነ-ውበት ፤የሞግዚትነት ወይም የህጻናት ክብካቤ ፤የመስተንግዶ፤የአሌክትሪክና የሸክላ የእንጨት ስራዎች፤እንዲሁም የጋርመንት ስልጠና እና ሌሎች ዘርፈብዙ አገልግሎቶችን አካቷል፡፡ የግንባታ ጥራቱም እልፍ ሴቶችን ከአስከፊው የወሲብ ንግድ ወይም ከጨለማ ህይወት አርነት በማውጣት የአዲስ ብሩህ ተስፋ ህይወት ብርሃን እንደሚያጎናጽፍ ብሎም ለከተማችን ብቻ ሳይሆን ለክልል መስተዳድር እህት ከተሞችም አንድ ምእራፍ ወደፊት የሚያሻግር ተግባራዊ ትምህርት እንደሚሰጥ ይጠበቃል፡፡


ይህ ማዕከል በክብርት ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ ሀሳብ አመንጪነት የብዙሀን ሴቶች መኖሪያ በሆነችው መዲናችን በተገቢው መንገድ ራሳቸውንና ቤተሰባቸውን መጥቀም ያልቻሉ
ከዚህም ባለፈ ለዘርፈ ብዙ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች የተጋለጡ መሆናቸውን በማስተዋል፣ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የረጅም ጊዜ ጥናት እንዲደረግበት አቅጣጫ በማስቀመጥና ለዘርፉ ምሁራኖች የተለያዩ ገንቢ ሀሳቦችን በማቅረብ ግንባታው ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ድረስ በመከታተል አላማውን ለማሳካት በሚያስችል መልከአ ምድራዊ አቀማመጥና ምቹ የአየር ንብረት ላይ እንዲገነባ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ይህ ፕሮጀክት በተለይም ክብርት ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ፣ የህብረተሰቡን ችግር በዘላቂነት ለመፍታት ሀሳቡን ከማመንጨት አንስቶ እስከ ማገባደጃው ባለው ሂደት በልዩ አይን ክትትል በማድረግ በ11 ወራት እንዲጠናቀቅ ያላሰለሰ ድጋፍና ክትትል በማድረግ፣ ችግር ፈቺ ሀሳብ የማፍለቅና ፕሮጀክቶችን የማስፈጸም አቅማቸውን በተግባር ያሳዩበት ነው፡፡ማእከሉ በውስጡ የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚሰጡ የየራሳቸው ኪነ-ህንጻዊ ውበት እንዲሁም የስፋትና የከፍታ ደረጃ ያላቸው ህንጻዎችን የያዘ፤ ዘመናዊ የስፖርት ማዘውተሪያ ሜዳዎችን፤ግዙፍ ኤልኢዲ ስክሪን የተገጠመለት የመዝናኛ አምፊ ቴአትር፤ የአትክልት እርሻ ማሳን ብሎም ከፍተኛ መጠን ያለው ንጹህ ውሃ የሚያቀርብ የራሱ የከርሰ ምድር ውሃ ጉድጓድ ከነ ግዙፍ ታንከሩ የያዘ ነው፡፡


ይህ ማዕከል የስርአተ ጾታ እኩልነትን ከማረጋገጥ እንዲሁም ለወደፊት አጠናክረን የምንከተለውን የፖለቲካ አቅጣጫ ከማመላከት አኳያ በመዲናችንም ሆነ በሀገራችን የመጀመሪያው ቢሆንም ተጨባጭ ውጤትና ስር ነቀል ማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ለውጦችን እንደሚያመጣ ጅማሬው ያመላክታል፡፡ በመሆኑም ከዚህ ተቋም የሚገኘው ተሞክሮ ተቀምሮና ሰፍቶ በአጭር ጊዜ ውስጥ በእህት ክልል መስተዳድር ከተሞችና በአጎራባች ሀገራት
ትምህርት የሚወሰድበት ተምሳሌት ፕሮጀክት እንደሚሆን አያጠራጥርም፡

ፕሉታርክ እንደጻፈው የሚከተለው አፈ-ታሪክ አለ።
ከክርስቶስ ልደት በፊት በ454 ዓመት፣ ኮሪዮሳኑስ የሚባል የሮማ ወታደራዊ መሪ ነበር። በጥንታዊ ሮም ታላቅ ወታደራዊ ጀግና ነው የተባለ ነበር። በርካታ ጦርነቶችን አሸንፏል። በዚህም አገሪቱን ከብዙ ጥፋት አድኗታል ተብሎለታል። ብዙውን ህይወቱን በጦር ሜዳ ስላሳለፈ በአካል የሚያውቁት ጥቂት ሮማውያን ብቻ ናቸው። በዚህ ምክንያት ከሞላ ጎደል ወደ አፈ-ታሪክነት ተለውጧል። አፈ-ታሪክ ታሪኩ እነሆ።


በ454 (ከክ.ል.በፊት) ወታደራዊ መሪ ኮሪዩሳኑስ የጦር ሜዳ ዝናዬንና ስሜን ተጠቅሜ ፖለቲካው ውስጥ ልግባ ሲል አሰበ። ከፍተኛ የምክር ቤት እንደራሴ ለመሆን ለሚያበቃው ቦታም የምርጫ ተወዳዳሪ ሆኖ ቀረበ። የምርጫ ተወዳዳሪዎች ወደተወለዱበት ቦታ ሄደው፣ ለጎሳቸው ሰው ንግግር ማድረጋቸው የዚያን ጊዜ ባህላዊ ህግ ነበርና፤ ኮሪዮላኑስም ወደ ህዝቡ ቀርቦ 17 ዓመት ሙሉ ለሮም ሲታገል በጦር ሜዳ በጥይት የተመታባቸውን ከደርዘን በላይ የሆኑትን የሰውነቱን ጠባሳዎች እየገለጠ አሳየ። ከዲስኩሩ ይልቅ ህዝቡን እንባ በእንባ ያደረገው የሰውነቱን ጠባሳዎች ማየት ነበር። ኮሪዮላኑስ በምርጫው እንደሚያሸንፍ እርግጠኛ መሰለ።
የምርጫው ቀን ሲደርስ ኮሪዮላኑስ በድፍን የምክር ቤት አባላትና በከተማው መኳንንት ታጅቦ ወደ ምርጫው ጣቢያ ገባ። ተራው ህዝብ ይሄ ሁሉ ጉራና እመረጣለሁ የሚል ልበ-ሙሉነት ከየት መጣ አለ በሆዱ።


ኮሪዮላኑስ አብረውት የሄዱትን አብዛኛዎቹን ወገኖቹን የሚጥም ንግግር አደረገ። ሆኖም፤ ዲስኩሩ ዕብሪትና ድፍረት የተሞላበት ከመሆኑም በላይ፤ በምርጫው ያለጥርጥር እንደሚያሸንፍ፣ የጦር ሜዳ ድሎቹን እንደሚኮራባቸው የሚያሳይ ሲሆን፤ ለሱ የገዢ መደብ ወገኖች ብቻ የሚገቡ ቀልዶችን በመጨመር እየፎከረ፤ ተቃዋሚዎቹንም በንቀት በማንገዋጠጥና በቁጣ  እየወነጀለ፤ ቢመረጥ ለሮም የበለጠ ሀብት እንደሚያስገኝ ደሰኮረ። በዚህ ንግግሩ ህዝቡ የአፈ-ታሪክ ጀግናችን ይለው የነበረው ታላቁ መሪ ተራ ጉረኛ መሆኑን ታዘበ። የሁለተኛው የጉራ ንግግሩ ይዘት በአገሩ ናኘና ህዝቡ ይሄንንማ አለመምረጥ ነው ተባባለ። እንዳለውም ህዝቡ ኮሪዮላኑስን ሳይመርጠው ቀረ።
ኮሪዮላኑስ በመሸነፉ ተናዶ ወደ ጦር ሜዳው ተመለሰ። ይሁን እንጂ ያልመረጠውን ህዝብ እንደሚበቀለውና ልክ- እንደሚያገባው በምሬት ዛተ። ከጥቂት ሳምንታት በኋላ በትልቅ መርከብ ወደ ሮም የሚገባውን እህል ለተራበው ህዝብ በነፃ ለማደል የምክር ቤቱ አባላት አስበው በጉዳዩ ለመምከር ተሰባሰቡ። በመካከል ግን ድንገት ኮሪዮላኑስ ብቅ አለና መድረኩን ቀማቸው። ይህን እህል ማከፋፈል በአጠቃላይ ለከተማይቱ ጎጂ ነው ሲል ተከራከረ። ጥቂቶቹን አሳመነ። በዚያም አላበቃ። የዲሞክራሲን ፅንሰ-ሀሳብ ጭምር ኮነነው። የህዝብ ተወካዮቹንና አዲሶቹን ተመራጮች በማስወገድ የከተማዋን አገዛዝ ለቀድሞዎቹ ገዢዎች (ስፓትራሺያን) መስጠት ይኖርብናል ሲል ክፉኛ ተሟገተ።


የኮሪዮላኑስን የመጨረሻውን ንግግር ህዝቡ ሲሰማ ቁጣው ወሰኑን ጣሰ። የህዝቡ ተወካዮች ደግሞ ኮሪዮላኑስ ህዝቡ ፊት ይቅረብ አሉ። ኮሪዮላኑስ ግን አሻፈረኝ፣ ህዝብ ፊት አልወጣም አለ። ከተማይቱ በሁሉም አቅጣጫ በህዝብ አመጽ ተቀጣጠለ። ይሄኔ ምክር ቤቱ የህዝቡን እንቅስቃሴ በመፍራት እህሉ ይከፋፈላል በሚለው ላይ ወሰነ። ሸንጎው በዚህ ህዝቡን ያረጋጋና እፎይ ያለ መሰለው። ህዝቡ ግን ኮሪዮላኑስ ያነጋግረን! ይቅርታ ይጠይቀን! ማለቱን ቀጠለ። ከፀፀተውና ጠባዩን አሳምሮ ሀሳቡን የሚያነሳ ከሆነም ወደ ጦር ሜዳ እንዲሄድ እንደሚፈቅዱለት ተናገሩ።
በመጨረሻ ኮሪዮላኑስ ህዝቡ ፊት ቀረበና ንግግር አደረገ። በዝግታና ለስለስ ባለ ቃና ጀመረና ቀስ እያለ ወደ ይፋ ዘለፋ ተሸጋገረ። ቃናው ሁሉ የዕቡይ ሆነ። የህዝብን ክብር የናቀ ዲስኩር ሆነ። ሰውን ማዋረድ ጀመረ። እሱ የበለጠ በተሳደበ ቁጥር ደግሞ የህዝቡ ቁጣ የበለጠ ገነፈለ። በመጨረሻ በጩኸት አፉን አዘጉት።
ሸንጎው ኮሪዮላኑስን በማውገዝ የሞት ፍርድ ፈረደበት። ዳኞቹንም እንደተለመደው ከታሪፒያ ቋጥኝ ቁልቁል እንዲወረውርና የሞት ቅጣት እንዲፈፀምበት አዘዛቸው። ህዝቡንም ውሳኔውን ደገፈ። ሆኖም ፓትሪሺያንኖቹ ጣልቃ ገብተው በመደራደር የሞት ቅጣቱ ወደ “ዕድሜ ልክ ከሥራ መገለል” እንዲሻሻል ተደረገ። የሮማ ታላቅ የጦር መሪ፤ ሁለተኛ ሮማ ከተማ ድርሽ እንደማይል ተረዳው፣ ህዝብም መንገድ ላይ ወጥቶ በይፋ ጨፈረ። እንደዚህ ያለ ጭፈራና በዓል ከዚህ ቀደም በሮማ ታይቶ አይታወቅም። የሮማ ህዝቦች ወራሪ ጠላት ሲያሸንፉ እንኳን እንደዚህ ዓይነት ፌሽታ አድርገው አያውቁም።

***


ከ2000 ዓመታት በፊት የሆነን ነገር መለስ ብሎ ያስተዋለ አያሌ ትምህርት ያገኛል።
ስንቶቻችን ራሳችንን ደገምን? ስንቶቻችን ራሳችንን በአፈ-ታሪኩ ውስጥ እናያለን? ሁኔታዎችን ስናጤን ታሪክ ብቻ ሳይሆን አፈ-ታሪክም ራሱን ይደግማል ያሰኘናል። ራስንም ወደፊት ነው እየሄድኩ ያለሁት ወደኋላ? ብሎ መጠየቁ አይቀርም። ከትላንት እስከዛሬ ተጠይቀው በግማሽ-ጎፈሬ ግማሽ-ልጩ መልክ ተመልሰው ወይም ከናካቴው ሳይመለሱ ቀርተው፣ እስከዛሬ የሚያጨቃጭቁን አያሌ ጥያቄዎች ነፍስ-እየዘሩ፣ በአካል እየተፋጠጡን (“ዴጃ ቩ” (deja vu) እንደሚባለው) “የት ነበር ያየናቸው?” የሚያሰኝ ድግግም ስዕሎች ነበሩ ዛሬም አሉ። የድንበር ጥያቄ ትላንት ነበረ ዛሬም አለ። ሀሳብ የመግለፅ፣ የመሰብሰብ፣ የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ ጥያቄ… ትላንት ነበረ ዛሬም አለ። የሰብአዊ መብት ጥያቄ ትላንት ነበረ ዛሬም አለ። የብሔር ብሔረሰብ ጥያቄ ትላንት ነበረ ዛሬም አለ፤ ወዘተ የሚገርመው ግን ታሪክ-ሰሪዎቹና የፖለቲካ መሪ ተናዋዮቹም ችግር ከሞላ ጎደል መደገማቸው ነው። መፈክሮችና መዝሙሮች ሳይቀሩ ሲደገሙ ማየት አስገራሚ ነው።
ለጉድ የጎለተው ሁሉንም ይታዘባል።
ገጣሚው እንዳለው፤
“ሲጨልም ስንነቃ፣ ሲነጋ ስንተኛ
እንቅልፍ እንኳ ካቅሙ መች ሞላልን ለእኛ።
ዘመን ተዘባርቆ ዓመት ተዟዟረ
ህልምም ወደ ኋላ፣ ማየት ተጀመረ”
ገዢው ፓርቲ በሙሉ አቅም የሚመራበት ሁኔታ ሲጠፋና፤ አዳዲሶች ፓርቲዎች በተደራጀ ሁኔታ የመምራት ሁኔታ ላይ ካልሆኑ፣ ሀገር ወደፊት መራመድ አቅቷት ወደኋላ እንዳትመለስ፣ ሀገር-ወዳዶች ሁሉ የሁኔታውን አሳሳቢነት መገንዘብ አለባቸው። ምን አይነት እገዛ ያስፈልጋል? ምን አይነት አቅም መፍጠር ይገባል? ብሎ ማሰብ ወሳኝነት ይኖረዋል። መድረክ ላይ ባሉ ፓርቲዎች ላይ አቃቂር ከመሰንዘር ባሻገር የእኛ አስተዋፅኦ ምን ይሁን ማለት ደግ ነው። የወቅቱ ጥሪ ይሄው ነው።
ሶስት ታዋቂ ሰዎች ስለታሪክ እንዲህ ይሉናል።
ታሪክ ራሱን ይደግማል። የታሪክ ጸሐፊ ግን አንዱን ይደግማል። (ፊሊፕ ጉዳላ- እንግሊዛዊ ፀሐፊ)
ታሪክ ራሱን አይደግምም። የታሪክ ጸሐፊ ግን አንዱን ይደግማል። (የእንግሊዝ ጠቅላይ ሚኒስትር)
ታሪክ ራሱን ይደግማል። ከታሪክ ስህተቶችም አንዱ ይሄ ነው (ክላርንስ ዳሮው የፈረንሳይ ጠበቃ)
ታሪክ መልኩን እየለዋወጠ ራሱን ይደግማል። በየጊዜው ግን የሚያስከፍለን ዋጋ እየጨመረ ነው የመጣው።
(ቶማስ ቤይሌ አሜሪካዊ የታሪክ ባለሙያ)
እንግዲህ የሚሰማንን መውሰድ የእኛ ፋንታ ነው።
በ1966 ዓ.ም የነበረውን ህዝባዊ እንቅስቃሴ፣ በ1983 የነበረውን የሽግግር ሁኔታና ዛሬ በሪፎርም ማግስት ያለንበትን ወቅት በሚገባ ስናጤን፣ ወደኋላ እንድናይ የሚያመላክቱ የበዙ ሁኔታዎች ስዕል እናገኛለን። ይሄ ደግሞ አሳሳቢ ነው። “ከነገር ሁሉ ምን ትጠላለህ?” ቢለው “ወደ ትላንትና መመለስ” አለ፤ የሚባለው የዚሁ ማገናዘቢያ ነው።

በትግራይ ክልል፣ ምስራቃዊ ዞን፣ ሃውዜን ከተማ የሚገኝ በርካታ ዓመታትን ያስቆጠረ ቅርስ መዘረፉ ተሰምቷል። ቅርሱ በከተማዋ በሚገኘው እንዳ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ይገኝ እንደነበረ ተገልጿል።
ይኸው ቅርስ ከወርቅና በከፊል ከብር የተሰራ መስቀል መሆኑን አንድ ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የቤተ ክርስቲያኑ አገልጋይ ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል።
ከ125 ዓመታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረው ይህ መስቀል፣ በ1891 ዓ.ም. ራስ መኮንን ሃውዜንና አካባቢውን በሚያስተዳድሩበት ወቅት ለቤተ ክርስቲያኗ ያበረከቱት እንደነበር እኚሁ አገልጋይ ጨምረው አብራርተዋል። የቅርሱ መዘረፍ የታወቀው በቅርቡ ቢሆንም፣ ቅርሱ ከንብረት ክፍል እንዲወጣ የተደረገው ግን ሐምሌ 19 ቀን 2015 ዓ.ም. እንደሆነ አገልጋዩ ይናገራሉ።
ንብረቱ ከተቀመጠበት ክፍል የወጣው በቤተ ክርስቲያኗ ሰበካ ጉባዔ ዋና ጸሐፊው መልዓከ ብርሃናት አሸናፊ ወረስ ፈቃድ ሲሆን፣ የወጣበት ምክንያት ቅርሱን ለጎብኚዎች “ለማሳየት” በሚል እንደነበር እኚሁ አገልጋይ ተናግረዋል።


ይሁንና ለተወሰኑ ወራት በሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት ሳቢያ ለሞቱ ሰዎች የፍትሐት ጸሎት በብዛት ሲደረግ በመቆየቱ፣ የቅርሱን ሁኔታ ለማረጋገጥና የት እንዳለ ለማወቅ አጋጣሚው እንዳልነበር ጠቅሰዋል።
በመጨረሻም፣ መጋቢት 6 ቀን 2016 ዓ.ም ቀን የመስቀሉ አለመኖር ሊታወቅ መቻሉን አገልጋዩ ያወሳሉ። ይህንንም ተከትሎ፣ የቤተ ክርስቲያኑን ቄሰ ገበዝ ጨምሮ ሌሎች የቤተ ክርስቲያኗ አገልጋዮች ቅርሱን ለማፈላለግ ቢሞክሩም ሙከራቸው አለመሳካቱን ነው የሚያመለክቱት።
የቤተ ክርስቲያኗ አገልጋዮች ለፖሊስና ለትግራይ ክልል ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ ጥቆማ ማቅረባቸውን እኚሁ አገልጋይ ገልጸው፣ ነገር ግን ተገቢው ትኩረት እንዳልተሰጠው አስረድተዋል።
የዚህ መስቀል ሙሉ መረጃ በትግራይ ባሕል እና ቱሪዝም ቢሮ ተሰንዶ የተቀመጠ መሆኑን አዲስ አድማስ ከተመለከተው የቅርሱ መረጃ ለመረዳት ተችሏል።


አርበኛ ወይዘሪት ሆይ ከበደች ስዩምን የሚዘክር መርሃ ግብር በነገው ዕለት ቅዳሜ ግንቦት 3 ቀን 2016 ዓ.ም በወመዘክር አዳራሽ ታላላቆች በታደሙበት ይከናወናል፡፡ በተጨማሪም የአርበኛዋን አንጸባራቂ ገድል የሚያሳይ  አጭር ድራማም ለታዳሚው ይቀርባል፡፡


በታሪካችን ሂደት ሴቶች  ያላቸውን አስተዋፅኦ የሚዘክር ልዩ የፓናል ውይይት ከኪነ-ጥበባዊ ዝግጅቶች ጋር ታጅቦ እንደሚቀርብም አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡

በመርሃ ግብሩ ላይ ዶ/ር ዘካሪያስ አምደብርሀን፣ ሴቶችን ከኢትዮጵያ ታሪክ አንጻር የሚያስቃኝ ጥናታዊ ጽሁፍ የሚያቀርቡ ሲሆን፤ ወይዘሮ ዮዲት አምሀ አበራ ደግሞ  የሴቶችን የስነልቦና ጥንካሬና እንዴት ይበረታታሉ? በሚለው ላይ አተኩረው ጥናታዊ መረጃ ያቀርባሉ ተብሏል፡፡

 የህግ ባለሙያዋ ወይዘሮ ማሪያ ሙኒር ደግሞ  ሴቶች ከወንድሞቻቸው ጎን በመቆም  እንዴት የለውጥ ሀዋርያ ይሆናሉ? በሚለው ላይ ሀሳብ ያጋራሉ፡፡ የጅማ ዩኒቨርሲቲ የአንደኛ አመት ተማሪ  ኤልዳና ዮሀንስ በበኩሉ፤ አዲሱ ትውልድ ምን ይጠበቅበታል? በሚለው ላይ ጠንካራ ሀሳብ  እንደሚያቀርቡ ይጠበቃል፡፡

በነገው ዕለት የሚታወሱትና የሚዘከሩት አርበኛ ወይዘሪት ሆይ  ከበደች ስዩም፤ የዛሬ 83 አመት በተደረገው የኢትዮጵያና የጣሊያን ጦርነት ላይ  ከፍተኛ የድል መንፈስ የነበራቸውና በጦር ሜዳው ላይም በጀግንነታቸው የተወደሱ ነበሩ፡፡

  ባለፉት 50 ዓመታት ከ8ሚ. በላይ ዜጎችን መድረስ ችሏል

  በአሁኑ ወቅት 700ሺ ዜጎች የፕሮጀክቱ  ተጠቃሚዎች ናቸው

  ትልቅ የሀገር ሃብት ነውና መከበርና መጠበቅ አለበት ተብሏል



ላለፉት አምስት አሰርት ዓመታት የቤተሰባቸውን እንክብካቤ ያጡና የቤተሰባቸውን እንክብካቤ ለማጣት በአደጋ ላይ ያሉ ህፃናትን የቤተሰብ እንክብካቤና ጥበቃ አግኝተው እንዲያድጉ ለሁለንተናዊ ዕድገታቸው የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ በማሟላት እንክብካቤ በመስጠት የሚታወቀው ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ፤ የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት በዓል  በይፋ ማከበር ጀመረ።

ድርጅቱ በእነዚህ አመታት፤ በአማራጭ የቤተሰብ ክብካቤ፣ በቤተሰብና ማህበረሰብ አቅም ግንባታ፣ በአስቸኳይ ጊዜ ሰብአዊ ድጋፍ እንዲሁም በትምህርት በጤናና በወጣቶች ማብቂያ ፕሮግራሞች ከ8ሚ. በላይ ዜጎችን መድረስ እንደቻለ ባወጣው መግለጫ አመልክቷል፡፡  

ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ የተመሰረተበትን የ50ኛ ዓመት ክብረ-በዓል  አስመልክቶ በዛሬው ዕለት ረፋዱ ላይ በድርጅቱ ዋና መ/ቤት ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል።

የኤስ ኦ ኤስ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ዳይሬክተር አቶ ሳህለማርያም አበበ ክብረ-በዓሉን አስመልክተው ሲናገሩ፤ ”ለ50 ዓመታት በቁርጠኝነት ፣በፍቅርና በብዙ ለውጦች የታጀበውን ክብረ በዓል ለማክበር በመብቃታችን ታላቅ ኩራት ይሰማናል።” ብለዋል፡፡

“ድርጅቱ ዛሬ የደረሰበት የስኬት ምዕራፍ የሰራተኞቻችን፣ የለጋሾቻችን፣ አጋሮቻችንና የምናገለግላቸው ማህበረሰቦች የጋራ ጥረትና የማያቋርጥ ድጋፍን የሚያንፀባርቅ ነው። በራስ መተማመንና በጥንካሬ የገጠሟቸውን ተግዳሮቶች ሁሉ አልፈው የትናንት ህፃናት የዛሬዎቹን ብርቱ ወጣቶች ማሳያ ነው።” ሲሉም አክለዋል፡፡


ያለፉት ዓመታት የልማት ስራዎቹንና ስኬቶቹን ለመዘከር ዓመቱን ሙሉ የሚከወኑ የተለያዩ የድርጊት መርሃ ግብሮችን ማዘጋጀቱን የገለፀው ኤስ ኦ ኤስ፤ ክብረ በዓሉ የድርጅቱን  ስኬቶችን ለማንፀባረቅ፣ ያበረከተውን  አስተዋፅኦ በጉልህ ለማሳየት፣ ድርጅቱን ያገለገሉትን ሰራተኞችና ደጋፊዎቹን ዕውቅና ለመስጠት እንዲሁም በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የሚገኙትን ህፃናት ለማገልገል ያለውን ቁርጠኝነት ለማሳየት ዕድል እንደሚሰጠውም አመልክቷል።

በ1966 ዓ.ም በአገራችን ለተከሰተው ድርቅ ከመንግስት ለቀረበለት ጥሪ ምላሽ ለመስጠት ወደ ኢትዮጵያ የገባው ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ፣ የመጀመሪያ ሥራውን በመቀሌ የጀመረ ሲሆን፤ ዛሬ አገልግሎቱን አስፋፍቶ በ 9 ክልሎች ውስጥ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

የኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ፣ “ህፃናት በፍቅር በሰላምና በሙሉ ዋስትና ሲያድጉ ማየት” የሚል ራዕይ ያነገበ መሆኑን የሚናገሩት ዳይሬክተሩ፤ምንም እንኳን ዋና  የትኩረት አቅጣጫዎቹ ህፃናት ቢሆኑም ቅሉ በአሁኑ ወቅት በማህበረሰብ ልማት ላይ በስፋት ተሰማርቶ እንደሚገኝ ጠቁመዋል፡፡

በአንድ የኢመርጀንሲ ፕሮጀክት ወደ ስራ የገባው ድርጅቱ፤ ዛሬ 41 ፕሮጀክቶች ላይ እየሰራ እንደሚገኝና  ከእነዚህ ውስጥ 7ቱ ብቻ የህፃናት ፕሮጀክቶች እንደሆነ ይገልፃል። የኤስ ኦ ኤስ ዳይሬክተር እንዳስረዱት፤ የቀሩት የማህበረሰብ ልማት ፕሮጀክቶች ናቸው።



 ድርጅቱ በህፃናትና ቤተሰብ ላይ አተኩሮ ከሚያከናውናቸው ጉልህ ስራዎች ጎን ለጎንም፣ የወጣቶች ልማትና የስራ ፈጠራ፣ የአደጋ ጊዜ እርዳታ፣ የትምህርትና ጤና ስራዎችም ላይ በስፋት እንደሚሳተፍ ለማወቅ ተችሏል።

የኤስ ኦ ኤስ አመራሮች የ50ኛ ዓመት ክብረ በዓላቸውን አስመልክተው በዛሬው ዕለት ለመገናኛ ብዙሃን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ከሴቶች ህፃናትና ወጣቶች ሚኒስቴር እንዲሁም ከሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን ተወክለው የተገኙ ሃላፊዎች ስለ ድርጅቱ በጎ ሥራዎች  ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል።

በአገሪቱ ህጋዊ ፍቃድ ተሰጥቷቸው ከሚንቀሳቀሱ 5ሺ የሚደርሱ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች መካከል ኤስ ኦ ኤስ ተጠቃሽ ነው ያሉት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ባለስልጣን  ም/ዳይሬክተር ፤ድርጅቱ በስራውም በምግባሩም የተከበረና የተደነቀ ነው ብለዋል።

የኢትዮጵያው ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች  በግዙፍነቱ በአለማቀፍ ደረጃ የሚጠቀስ ነው ያሉት ም/ ዳይሬክተሩ፤ ትልቅ የአገር ሃብትና ተቋም በመሆኑ መከበርና መጠበቅ አለበት ብለዋል።

 ኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች በኢትዮጵያ እ.ኤ.አ ከ1949 ጀምሮ የቤተሰብ እንክብካቤ ላጡ ህፃናት በፍቅር የተሞላ ቤተሰብ ሲሰጥ የቆየው የዓለማቀፉ የኤስ ኦ ኤስ የህፃናት መንደሮች ፌዴሬሽን አካል ነው።  ኤስ ኦ ኤስ በመላው ዓለም በ132 አገራት የሚንቀሳቀስ ሲሆን በዓለማቀፍ ደረጃ የተመሰረተበትን 75ኛ ዓመት  እያከበረ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ነዋሪነታቸውን በአሜሪካ ያደረጉት  አቶ ጥበበ እሸቱ ለመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል ከ2.5 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ የቁሳቁስ ድጋፍና ለ7ሺ500 አረጋውያን ሙሉ ወጪውን በመሸፈን የምሣ  ማብላት መርሃ ግብር አከናውነዋል፡፡  

አቶ ጥበበ ትላንት ሚያዝያ 29 ቀን 2016 ዓ.ም በመቄዶንያ ማዕከል በመገኘት አረጋውያኑን ምሣ ያበሉ ሲሆን፤ በርካታ ብርድልብሶችንና ጫማዎችንም ለማዕከሉ አበርክተዋል፡፡

ድጋፉን በማድረጋቸው  ደስተኛ መሆናቸውን የገለጹት አቶ ጥበበ እሸቱ፤ ቀጣይነት ያለው ድጋፍ ለመቄዶንያ የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል ለማድረግም ቃል ገብተዋል።

ከዚህ ቀደም ደቡብ ወሎ ጋሸና አካባቢ በጦርነቱ ምክንያት ለተፈናቀሉ ሰዎች 150 ቤቶችን ሰርተው ያስረከቡት በጎ አድራጊው አቶ ጥበበ፤በቅርቡም በትግራይና በአማራ ክልል ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖች ድጋፍ ለማድረግ ቅድመ ዝግጅት ማጠናቀቃቸውን ተናግረዋል፡፡

መቄዶንያ የበጎ አድራጎት ማህበር ምንም ጧሪና ደጋፊ የሌላቸውን በተለይም ደግሞ እራሳቸውን ችለው መንቀሳቀስ፣ መመገብና መፀዳዳት የማይችሉ የአልጋ ቁራኛ የሆኑና የሰው ድጋፍ የሚያስፈልጋቸው አረጋውያንንና አዕምሮ ሕሙማንን ከወደቁበት ጎዳና ላይ በማንሳት ከ7,500 በላይ የሚሆኑ ተረጂዎችን በአዲስ አበባ፣ ደሴ፣ ድሬዳዋ፤ ሻሸመኔ፣ አድዋ፤ ባህርዳር፣ ሐረር፤ ጋምቤላ እና ጎሬ፣ መቱ፣ ጂማ፤ ሰንዳፋ በኬ፣ ሐዋሳ፣ አሶሳ፣ ጎንደር፣ ደብረማርቆስ፣ አምቦ፣ ኮረም፣ ሰመራ፣ ሰቆጣ፣ አምደወርቅ፣ ላሊበላ፣ አዲስ ዘመን፤ አምቦ እና አርባምንጭን ጨምሮ በአጠቃላይ በ25 ከተሞች ውስጥ በመደገፍ ላይ  ይገኛል።

በቀጣይም በወሊሶ፣ ሱልልታ፣ ሰበታ፣ ደብረ ብርሃን፤ ሆሳዕና፣ ዲላ፣ ጂግጂጋ  እና በሌሎች የሀገሪቱ ከተሞች ላይ የበጎ አድራጎት ተግባሩን ለማከናወን  ከወዲሁ እንቅስቃሴ መጀመሩን ለማወቅ ተችሏል፡፡

በአንድ በረሀ ውስጥ ሁለት ሰዎች በፈረስ ሆነው ሜዳውን አቋርጠው በመሄድ ላይ ሳሉ ይገናኛሉ። ከሁለቱ የአንደኛው ፈረስ አንካሳ ነው። ባለ አንካሳው ፈረስ በረሀውን አቋርጦ አለሙ አገር ለመድረስ ፈረሱ አላስተማመነውም። ስለዚህም እንደምንም ብሎ ደህነኛውን ፈረስ ከሌላው ሰውዬ ለመውሰድ መላ ይፈልግ ጀመር።
በመጨረሻም እንዲህ አለው፡-
“ወዳጄ ሆይ፤ ፈረሶቻችን ከእኛው ጋር ለብዙ ጊዜ የኖሩ በመሆናቸው ጨክነን በአለንጋ አንገርፋቸውምና ፈጥነው ለመሄድ ዳተኝነት ይሰማቸዋል። ስለዚህ እንቀያየርና እንደልብ እየገረፍናቸው በረሀውን ፈጥነን እናቋርጥ።”
ባለ ደህነኛው ፈረስም ይህን አግባብ ያልሆነ የብልጠት ጥያቄ በብልሃት ሲመልስ፤
“ጥያቄህ መልካም ነበር። ነገር ግን የእኔ ፈረስ እንዳንተ ፈረስ ዳተኝነት የለበትምና ማንም እንዲገርፈው አልፈቅድም። የአቅሙን ያህል፣ ባለው ፍጥነት በረሀውን እያቋረጠ በመሄዱ ፈረሴ አንዳችም አለንጋ ሊያርፍበት አይገባም፤ የጭካኔ ተግባርም ሊፈፀምበት ተገቢ አይደለም” አለው።
ባለ አንካሳው ፈረስ ዘዴው ባለመሥራቱ ተናዶ ጠብ ለመጫር ፈለገ። ስለዚህም፣
“እኔ ነኝ ጨካኝ? ለሁለታችንም ጥቅም ባሰብኩ ጨካኝ ትለኛለህ? በጭራሽ ጭንቅላት የሌለህ ደደብ ሰው ነህ!” ሲል ነገር ጀመረው።
አንድ ሁለት ሲሉ ወደ ድብድብ ተሸጋገሩ። ባለ አንካሳው ፈረስ ጡንቻው ፍርጥም ያለ ነበርና ባለ ደህነኛውን ፈረስ በትግል ጥሎ፣ ፈረሱን ነጥቆት፣ የሱን አንካሳ ፈረስ ጥሎለት እየጋለበ ሄደ።
በትግል የተሸነፈው ሰው ግን ተስፋ ሳይቆርጥ ከወደቀበት ተነስቶ አንካሳው ፈረስ ላይ ወጥቶ መንገድ እያቆራረጠ ከሚቀጥለው መንደር ቀድሞ ገብቶ ለዳኛ ከሰሰው። የሰው ፈረስ የወሰደው ሰው ከዚያ መንደር ሲደርስ በዳኛ ተያዘና ተጠየቀ።
“ፈረሱ የገዛ ራሴ ፈረስ ነው። ያሳደግሁት፣ አብሮኝ የኖረ ፈረሴ ነው። ይሄንንም ሰው እንኳን ፈረስ ልወስድበት ዓይኑንም አይቼው አላውቅ!” ሲል ፍርጥም ብሎ መለሰ።
ዳኛው ሽማግሌና አስተዋይ ሰው ናቸው። ነገሩ የጉልበት ስራ እንዳለበት ገብቷቸዋል። ሆኖም ለተሰራው ተንኮል ምንም ማስረጃ አልነበራቸውምና ብዙ ካሰቡ በኋላ አንድ ዘዴ ታያቸው።
“በሉ ሁለታችሁም ፊታችሁን ዞራችሁ ቁሙ”
ሰዎቹ እንደተባሉት አደረጉ።
ዳኛው በርኖሳቸውን አውልቀው የደህነኛውን ፈረስ ፊት ሸፈኑት። ከዚያም ሰዎቹ እንዲዞሩ አዘዙና ያንን የሰው ፈረስ የነጠቀ ጉልበተኛ ፊቱ ወደተሸፈነው ፈረስ እያሳዩ እንዲህ ሲሉ ጠየቁት፡-
“ለመሆኑ ይሄ ፈረስ የግራው ነው የቀኝ ዐይኑ የታወረው?”
 ያም ጉልበተኛ ሰው ድንገተኛ ጥያቄ ስለሆነበትና ካልመለሰም እንደሚጋለጥ በማሰብ፤ በአቦ-ሰጡኝ
“የቀኝ ዐይኑ ነው!” ሲል መለሰ።
ዳኛውም በርኖሱን ከፈረሱ ፊት ገልጠው፤
“ይገርማል! ፈረሱ ዕውር ይሁን አይሁን እንኳ ሳታውቅ ነው፣ የእኔ ፈረስ ነው የምትለው። ፈረሱ ሁለቱም ዐይኑ ደህና ነው። ካንተ ጋር የኖረ ፈረስ ቢሆን ኖሮ ጥያቄውን በተገቢ መልኩ በመለስህ ነበር። ሆኖም የሰው ገንዘብ ነውና ልታውቀው አልቻልክም”
በማለት ፈረሱ ለባለቤቱ እንዲመለስለት አደረጉ።

***
“መውደዱ ጠንቶ አድልዎ ዕውር እንዳያደርገን፣
ጥላቻው ከሮ ህሊና እንዳያሳጣን እንጠንቀቅ” ብሏል አንድ ያልታወቀ ደራሲ። በየትም ቦታ፣ በማናቸውም ጉዳይ ላይ ብልሃትና እውቀት ከሌለ ዳኝነት መስጠት ከባድ ኃላፊነት፣ ከባድ ሥራ ነው። የተጣሉ ልጆች የተጣሉ ባልና ሚስት ከማስታረቅ ጀምሮ ተፎካካሪ ባለሙያዎችን አወዳድሮ ፍርድ እስከመስጠት ድረስ ርቱዕ ዳኝነት የሚሻ ጉዳይ ነው።
ትክክለኛ ዳኝነት በግፍ የሰው ንብረት እንዳይጠፋ፣ እንዳይወሰድ፣ አይጥ በበላ ዳዋ እንዳይመታ፤ ጉልበተኛ ደካማውን እንዳያጠቃ፣ መብት እንዲከበር፣ መልካም የሰራ እንዲመሰገን እንዲነሳሳ፣ ክፉ የሰራ እንዲወቀስ አለመሥራቱን እንዲያውቅ ያደርጋል። ለዚህ ደግሞ ተገቢውን ዳኝነት ለመስጠት የሚችሉ አስተዋይ ብልህ ዳኞች ያስፈልጋሉ። በተለይ ሽልማት የሚሰጥበት ዳኝነት ሲሆን ደግሞ፣ ከማቴሪያል እሴቱም ይልቅ ስም (ስምም ቢሉ ሙያዊ ስም) አለበትና የሽማግሌ እርጋታና ስክነት ያላቸው መክረው ዘክረው፣ አውጥተው አውርደው፣ ግራ ቀኙን አይተው፣ ያለ አድልኦ፣ ያለ ወገናዊነት ፍርድ የሚሰጡ ሰዎች ያስፈልጉታል። ይህን ሳያሟሉ አንድም ያለዕውቀት አንድም በድፍረት አሊያም በንዝህላልነትና ያለብስለት ተነስተው የተጣላ እናስታርቅ የሚፎካከርን እንዳኝ፣ ብርቱና ሰነፉን እንለይ ቢሉ፣ “ለራሱ ያልተገረዘ የሰው ዐይን ይይዛል” የተባለው ዓይነት ይሆናል።
መልካም ዳኛ ተገኝቶ፣ ሚዛናዊ ዳኝነት እንዲኖር የማስፈለጉን ያህል ደግ ያደረገን የሚያበረታታ ማሕበረሰብ መኖሩ ዋና ነገር ነው። ከአያሌ አሉታዊ ነገሮች መካከል ጥቂት አዎንታዊ ፋይዳዎችን አንጥሮ አውጥቶ እነሱን ለማጉላት የሚሞክር ህብረተሰብ፣ ለነገ የወደፊት ገንቢ ጥርጊያ መንገድ እንዲኖር ከወዲሁ ተመክሮውን ያነቃል። ጨለማ ከከበባት ህይወት መካከል ጥቂት የብርሃን ፍንጣቂ ሲያገኝ፣ ለዚያች ሰፊ ቀዳዳ የሚያበጅ ህብረተሰብ፣ ራእዩ ግቡን እንዲመታ የተለያየ መንገድ ይከሰትለታል። የሀሳብ አማራጭ፣ የመኖር አማራጭ፣ የትግል አማራጭ ይኖረዋል። ስለ ዛሬ ጨለማ ሳይሆን ስለ ነገ ብሩህ ህይወት ለማለም የአእምሮ ጭጋግ አይጫነውም። “የሚገድል ጦር ተኝቶም ይወጋል” ይሏልና ከመሰረቱ ቀና የሆነ ዜጋ የሚበጀውን ከጧቱ ማየት የነገውን በልበ-ሙሉነት መቅረጽ ለሰው፣ በህይወቱ እያለ ዋጋውን መስጠት፣ ለመልካም ስራ ወቅታዊ ውዳሴን አለመንፈግ አሉታዊ ማህበረሰብ ከመሆን ያድነናል። በዚህ መንገድ ጀግና ይፈጠራል። ኮከብ ይበራል። ለሀገር ዐይን የሚሆኑ ሰዎች ይፈልቃሉ - ይበቅላሉ - ይፀድቃሉ።
ግልጽ፣ የተረጋጋና ዲሞክራሲያዊ ህብረተሰብ እንዲኖር ቀና ቀናውን እንጂ ክፉ ክፉውንና ጉድፍ ጉድፉን ብቻ የሚያይ መሪ፣ ድርጅት፣ ፓርቲ አይደለም እሚበጀው። ከትንሿም እንቅስቃሴ ውስጥ ቢሆን ደግ ደጓን የሚያይ እንጂ መጥፎ መጥፎውን እሚያይ፣ ክፉ ክፉውን እሚያወራ ሰው ወንዝ አያሻግርም። አገር አያለማም። ህዝብ አያሳድግም። በመርፌም የሚለቀም ቢሆን ከእኛ ውጪ ባለው ሰው ወይም ቡድን ላይ ደህና ደህናውን ነገር መርጦ ማየት ከብዙ ደባ፣ ከብዙ መጠላለፍ፣ ከብዙ መጠፋፋት፣ ከብዙ ውድቀት ያድናል። የልብ አንካሳ እመንገድ ሲያድር፣ የእግር አንካሳ እቤቱ ደርሶ ያድራል እንደሚባለው መሆኑ ነው። ምን ነግሬ ላሳስቀው ከማለት ምን አድርጌ ላስለቅሰው የሚል ሲበዛ አሉታዊነት (Negativism) ይንሰራፋል። የሚሾም የሚሸለም ከማየት፣ የሚዋረድ የሚነጠቅ ማየት ያረካል። አሉታዊነት ሲከፋ አብሮ ማደግ ቀርቶ አብሮ መኖር የማያስችል አለመተማመንን ይፈጥራል። መግባባትን ያጨልማል። መቻቻልን ያዳፍናል። ፖሊሲ መቅረጽ፣ የአፈፃፀም አቅም መገንባት፣ ሙስና ማጥፋት፣ ድህነት ቅነሳ ሁሉም ያለ አዎንታዊ ፍቃደ-ልቡና፣ ያአመስጋኝና ወሮታ-ከፋይ ህብረተሰብ (Merit-Giving Society) አንድ ጋት አይራመድም።
ክፉ ክፉውን የሚያይ ሹም፣ ጉድፍ ጉድፉን የሚለቅም ባለስልጣን ለራሱ ብዙ ነጥብ ይሰጣልና ውሎ አድሮ ሌላውን ሁሉ አኮስሶ እያየ፣ ካለ እኔ ማን አለ ማለቱ አይቀርም። ህብረተሰቡም የእሱን ክፉ ስለሚመኝና የእሱን ጎዶሎ ስለሚፈልግ እንቅፋት ሲደረድርለት፣ መቃብር ሲምስለት፣ ቀን ሲጠብቅለት ነው የሚኖረው። በአሉታዊ ህብረተሰብ ውስጥ ሹሙ ከዜጋው፣ ደንጊያው ከቅሉ እንደተጋጨ እንደተላተመ ነው የሚከርመው። በእንዲህ ያለው ጊዜ ሰላም ይጠፋል። ሠርቶ ማደር ያቅታል። “ማክቤዝ እንቅልፍን ገደላት” እንዲል ሼክስፒር፣ ሹሙ ሁሉ በግፉ፣ በሙስናው፣ በአድሎአዊነቱ፣ በማን-አለብኝነቱ… ምክንያት እንቅልፉን ያጣል። ውሎ አድሮም ከዚህ ቀደም እንደታዩት ሹማምንት እዚያው የውድቀት ጉድጓድ ውስጥ ይገባል። ማህበረሰቡም የእጁን አገኘ ይለዋል። ከወደቀውም ሆነ ከራሱ ለነገዬ ብሎ የሚያኖረውም የእርምት ስንቅ የለም። ለአዲስ ሹም አጨብጭቦ፣ ደሞ ነገ ጥምብ- እርኩሱን አውጥቶ አንቅሮ ይተፋዋል። “ዛሬ ፈጥሮ ነገ ቀብሮ” እንዳለው ነው ደራሲው።
ህብረተሰብ ለእድገት እንዲሰለፍ አሉታዊ ባህሪን ማስወገድ አለበት። አዎንታዊ አስተሳሰብን (Positivism) ማዳበር አለበት። መልካም የሰራን ለማበረታታት፣ ለላቀ ለመሸለም፣ ያለ አድልዎ ለመፍረድ፣ ከልብ ለመደገፍ፣ ከልብ ለመንቀፍ፣ ግልጽ ለመሆን ሁኔታዎች መመቻቸት አለባቸው። ከጽንፍ ወደ ጽንፍ ከመሄድ ይልቅ ሌላ አማካይና አማራጭ መንገድ ማየት ይገባል። ያለ ብሔረሰባዊ መንገድ የትም አልሄድም ብሎ ተከርሞ ድንገት የባነኑ እለት ብሔረሰብ ይውደም ወደማለት ከተሄደ አደገኛ ጽንፈኝነት ይሆናል።
ማንም ይሁን ማን ለረዥም መንገድ ከተነሳ ሆደ-ሰፊ መሆን አለበት። ለዚህም የተቻለው ጥረት ሁሉ ሊደረግ ይገባል። በተለይ ኃላፊዎች፣ ሹሞች፣ ባለአደራዎች፣ መሪዎች ጥብቅ አደራ የሚጣልባቸው ናቸው። አለበለዚያ ይህ ሳይኖራቸው በስሜታዊነትና በማን-አለብኝ ከተዋጡ፣ ለራሱ ያልዳነ ለአማቱ መድኃኒት ይቆርጣል እንደተባለው ይሆናልና ከወዲሁ እናስብበት።
ፋሲካውን በአዳዲስ ሃሳብ እንፈስክ!!
መልካም የትንሳኤ በዓል!!

የፍየል ዋጋ አይቀመስም - የበግ ቅናሽ አሳይቷል

የትንሳኤ በዓል የገበያ ዋጋ ከገና በዓል የገበያ ዋጋ አንፃር መጠነኛ መሻሻል ማሳየቱን ነጋዴዎችና ሸማቾች ተናገሩ፡፡ የአዲስ አድማስ ሪፖርተሮች በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ ትልልቅ የገበያ ቦታዎችን ከቃኙ በኋላ ባገኙት መረጃ ነው የበዓል ግባቶች የዋጋ ሁኔታ  መጠነኛ  መረጋጋት ማሳየቱን ማረጋገጥ የቻሉት።  ነጋዴዎችና ሸማቾች እንደገለፁት፤ ለገና በዓል ገበያ የ1 ኪሎ የሽንኩርት ዋጋ 150 ብር የነበረ ሲሆን ሰሞኑን አንድ ኪሎ ቀይ ሽንኩርት ከ55-60 ብር እየተሸጠ ይገኛል። ለገና 11 እና 12 ብር የነበረው የፈረንድ እንቁላል አሁን በዘጠኝና በ10 ብር እየተሸጠ ይገኛል። ምንም እንኳን በዓሉ ከመቃረቡ በፊት የፈረንጅ እንቁላል ሰባት ብር ከሀምሳ ሲሸጥ የቆየ ቢሆንም አሁን ከ9-10 ብር መሸጡ ከገናው በዓል የዋጋ ሁኔታ አንፃር የተሻለ መሆኑን ሸማቾች ገልፀዋል። በስድስት ኪሎ፣ በመገናኛው ሾላ፣ በሰሜን ማዘጋጃው ሾላ ገበያ፣ በሀይሌ ጋርመንትና በፈረንሳይ አካባቢ በሚገኙ ገበያዎች የተዘዋወሩት የአዲስ አድማስ ሪፖርተሮች ለመቃኘት እንደሞከሩት፣ የዓመት በዓል ፍጆታዎች ዋጋ ከቦታ ቦታ መጠነኛ ለውጥ እንዳለው ለመታዘብ ችለዋል፡፡
በ6 ኪሎ አትክልት ተራ ቀይ ሽንኩርት 60 ብር፣ ካሮት 80 ብር፣ ነጭ ሽንኩርት 360 ብር፣ ሎሚ በኪሎ 250 ብር፣ ድንች 40 ብር እየተሸጠ ሲሆን ፈረንሳይ አካባቢ ትልቁ የወላይታ ዶሮ ከ1 ሺህ 300 እስከ 1 ሺህ 700 ብር ድረስ ለገበያ ቀርቧል፡፡ 5 ሊትር ኦማር ዘይት 1 ሺህ 150 ብር እየተሸጠ ሲሆን የ100 ብር ጭማሪ አሳይቷል።
መጠነኛና አነስ ያሉ የፈረንጅ ዶሮዎች ከ1 ሺህ 100 ብር ጀምሮ እየተሸጡ ሲሆን፣ የዳቦ ዱቄት አንደኛ ደረጃው በኪሎ 1 መቶ ብር እየተሸጠ ሲሆን፤ አንደኛ ደረጃ የሸኖ ቅቤ ለጋው 900 ብር መካከለኛው 800 ብር እንዲሁም በሳሉ 690 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
በመገናኛው ሾላ የገበያ ቅኝታችን ደግሞ  አንድ ኪሎ ቀይ ሽንኩርት ከ40-70 ብር፣ ነጭ ሽንኩርት ከ350 እስከ 400 ባሮ ሽንኩርት በኪሎ 45 ብር እየተሸጠ ሲሆን፤ በተለይ ነጭ ሽንኩር በአዘቦት ቀናት ሲሸጥበት ከነበረው ዋጋ በጣም መወደዱን ሸማቾች ተናግረዋል።  በዚሁ በመገናኛ ሾላ ገበያ የሀበሻ ዶሮ ከ1 ሺህ 200 እስከ 1 ሺህ ሰባት መቶ ብር ሲሸጥ፣ የፈረንጅ ዶሮ ከ1 ሺህ 100 እስከ 1 ሺህ 600 ብር ድረስ እየተሸጠ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ መካከለኛ የፈረንጅ ዶሮ ከ800 እስከ 850 ብር እየተሸጠ መሆኑንም የሾላን ገበያ የቃኘው ሪፖርተራችን ገልጷል፡፡
በፈረንሳይ የበዓል ገበያም ሆነ በሾላ ገበያዎች  ዶሮ እዚያው ገዝቶ እዚያው የማሳረድ ባህል እየተስፋፋ ሲሆን ምንም እንኳን በቅኝታችን ወቀት ገና ፆሙ ያልተፈታ  ባለፈው ገና አንድ ዶሮ አርዶ ለመገንጠል ከ3-5 ደቂቃ እንደሚፈጅና ለአንድ ዶሮ 100 ብር ያስከፍሉ እንደነበር አረጋግጠናል፡፡ በሾላ ደግሞ ከ50 ብር እስከ 150 ብር ለዶሮ አራጅ እንደሚከፈል ሸማቾች ተናግረዋል፡፡
በሾላ ገበያ የሸኖ ቅቤ ለጋው በ950 ብር የሚሸጥ ቢሆንም ሲሆን፤ መካከለኛው 850 ብር፤በሳል ቅቤ በ750 ብር እየተሸጠ ነው። በበዓል ገበያ ቅኝታችን በሾላ ገበያ ካገኘነው የበዓል ግብአት ውስጥ ለጠላ የሚሆን የተመጣጠነ ውህድ ዱቄት (ጌሾ ብቅል፣ አሻሮ ተዘጋጅቶ የተቀላቀለ) ሲሆን፤ 1 ኪሎ ግራም የታሸገ የጠላ ምጥን 200ብር እንደሚሸጥ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከጠላ ምጥኑ ጎን ለጎን ደግሞ አልኮል የሌለውና ከገብስ ብቻ የሚዘጋጀው “ኬኔቶ” (መውደድ) ለሚባለው መጠጥ የሚውል አረር ተደርጎ የተቆላ ገብስ በ1 ኪሎ ግራም መጠን ታሽጎ እንዲሁ በ200 ብር እየተሸጠ ይገኛል፡፡
አዲስ አድማስ ሀይሌ ጋርመንት አካባቢ የሚገኘውን የበግና የፍየል ገበያ ለመቃኘትም ሞክሯል፡፡ በዚሁ ቅኝት ምንም እንኳን እንደቀድሞዎቹ የበዓላት ድባብ የደመቀና የደራ የገበያ እንቅስቃሴ ባናስተውልም፣ ነጋዴዎች ግን ከቀደሙት በዓላት የዋጋው ሁኔታ ጥሩ የሚባል መሆኑን ገልፀውልናል፡፡ ከገበያው በበዓሉ ዋዜማ እየደመቀ እንደሚሄድና የሸማቹ መጠን ይጨምራል የሚል ተስፋ እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡
በዚሁ የቁም እንስሳት የግብዓት ስፍራ አነስ የሚል በግ ከ6 ሺህ ብር ጀምሮ እየተሸጠ ሲሆን መካከለኛ መጠን ያለው ከ8-10 ሺህ ሙክት በግ ከ12 እስከ 15 ሺህ ብር እየተጠራበት እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡ የአሁኑ የበዓል ሰሞን የበግ ዋጋ ካለፈው ዓመትም ሆነ ካለፈው ገና የበግ ዋጋ አንፃር ቅናሽ እንዳለው ነው ነጋዴዎች የሚናገሩት አምና የመካከለኛ በግ ዋጋ 15 ሺህ ብር እንደነበር በማስታወስ፡፡
ዘንድሮ የፍየል ዋጋ ብቻ የሚቀመስ አይደለም የሚሉት ነጋዴዎ ትልቅና ሙክት የሚለው ፍየል እስከ 45 ሺህ ብር እየተጠራ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡
በካራሎ የቁም ከብት እንስሰሳት ቅኝት ያደረጉት የአዲስ አድማስ ሪፖርተሮች በዚህ ገበያ የበሬ ዋጋ ምን ያህል ነው በማለት ነጋዴዎችን ገዢዎችን ያነጋገሩ ሲሆን ከ80 ሺህ እስከ 200 ሺህ ብር ባለው የዋጋ መጠን እንደየአይነታቸውና እንደየመጠናቸው እየተሸጡ ነው፡፡ አነስተኛ የሚባለውና ከጥጃ ከፍ ያለው ወይፈን 30 ሺህ ብር እየተባለ ነው፡፡
በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተከሰተው የፀጥታ ችግር በሬ በግ፣ ዶሮና ፍየል እንደልብ ወደከተማ ለማምጣት አስቸጋሪ በመሆኑ ለገበያው መቀዛቀዝ አንዱ ምክንያት ሲሆን ከኑሮ ውድነቱ የተነሳ የሸማቹ የመግዛት አቅም በመዳከሙ ሌላው ለበዓል የገበያ ድባብ እንደምክንያት ተጠቅሷል በሸማቾችና በነጋዴዎች ከላይ የተጠናቀረው የገበያ ቅኝት ባለፈው ረቡዕና ጋዜጣው ማተሚያ ቤት እስከገባበት ሀሙስ ማታ ድረስ የተደረገ መሆኑን እየገለፅን ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች መልካም የትንሳኤ በዓል እንዲሆን እንመኛለን፡፡


በትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር አመራሮች መካከል፣ በፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት አፈፃፀም ዙሪያ፣ “ሰላም ፈላጊ እና ጦርነት ፈላጊ አለ” በሚል እየተፈጠረ ያለው የልዩነት ትርክት ስህተት ነው፤ ሲሉ የክልሉ ጊዜያዊ አስተዳደር  ምክትል ፕሬዚዳንት  ጄነራል ታደሰ ወረደ ተናገሩ፡፡
ጄነራሉ ባለፈው ረቡዕ ሚያዝያ 23 ቀን 2016 ዓ.ም  ለትግራይ ክልል መገናኛ ብዙኃን በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ የፕሪቶሪያ ግጭትን በዘላቂነት የማቆም ስምምነት አተገባበርን በተመለከተ ጊዜያዊ አስተዳደሩ ከፌደራል መንግስትና ከመከላከያ ሠራዊት ጋር የሁለት ቀን ውይይት ማድረጉን አመልክተዋል።
የፕሪቶሪያ ውል አተገባበርን በተመለከተ  በተደረገው  ውይይት፣ የአፈፃፀም ስምምነት ላይ ተደርሷል ያሉት ምክትል ፕሬዚዳንቱ፤ “ከውይይቱ የማጠቃለያ ስምምነት በመነሳት የትግራይ ደቡባዊ ዞንና ፀለምት እስከ ግንቦት 30 ቀን 2016 ዓ.ም.፤ የምዕራብ ትግራይ ጉዳይ ደግሞ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2016 ዓ.ም.  ዕልባት እንዲያገኙ የጋራ መግባባት ላይ ደርሰናል” ብለዋል።
ተፈናቃዮች በሁለት ወራት ውስጥ ወደቀያቸው  እንደሚመለሱ የገለጹት ጄነራል ወረደ፤ ተፈናቃዮቹ  ወደቀያቸው ከመመለሳቸው በፊት “መሬታቸው፣ ቤታቸውና እርሻቸው ተይዞ ስለሚገኝ በመጀመሪያ ምቹ ሁኔታ እንዲፈጠር” መግባባት  ላይ መደረሱን ጠቁመዋል፡፡
አያይዘውም፤ “ትጥቅ ማን ይፈታል ? እንዴትስ ይፈታል? የትኞቹ አስተዳደሮች ይፈርሳሉ? ተፈናቃዮች በምን መልኩ ይመለሳሉ?” በሚሉ ነጥቦች ላይ ውይይት ተካሂዶ ዝርዝር እቅድ እንደወጣለት ጠቅሰዋል።
 በትግራይ ጊዜያዊ አስተዳደር አመራሮች መካከል፣ በፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት አፈፃፀም ዙሪያ፣ “ሰላም ፈላጊ እና ጦርነት ፈላጊ አለ” በሚል እየተፈጠረ ያለው የልዩነት ትርክት ስህተት ነው  ያሉት ጄነራሉ፤ “ትርክቱ ስህተት መሆኑን ለፌደራል መንግሥት ገለፃ ሰጥተናል” ብለዋል፡፡ ይሁንና ጄነራሉ  እየተፈጠረ ነው  ያሉት የትርክት ስሕተት ከየትኛው ወገን እንደመነጨ በግልጽ አልተናገሩም፡፡
“የፕሪቶሪያው ውል ስምምነቱ ከተፈፀመበት ቀን ጀምሮ ከማንኛውም አይነት ግጭት በፀዳ መልኩ ተፈፃሚ ይሆናል ተብሎ ባይጠበቅም፣ አሁን መሬት ላይ ካለው ሁኔታ አንጻር  አንዳችም ለግጭት የሚጋብዝ ሁኔታ የለም” ያሉት  ጄነራሉ፤ “የፌደራል መንግስት በበኩሉ፣ የስምምነቱን ትግበራ እስከ ታች ድረስ እንደሚያወርደው እንጠብቃለን” ብለዋል፡፡  
ከሰሞኑ በራያ ወረዳዎች እና አላማጣ ከተማ እንደ አዲስ ከተቀሰቀሰው ግጭት ጋር ተያይዞ የተፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር ከ50 ሺህ ማለፉን  የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት (ኦቻ) አስታውቋል።

Page 1 of 705