Administrator

Administrator

አሳ ሁልጊዜ በመረብ ብቻ አይጠመድም፡፡ የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራሙ እንዲህ ያለ አሳዛኝ ውጤት በማስመዝገብ ሲከሸፍ፣ ብዙዎቹ ቤተእስራኤሎችና እነሱን ለመርዳት ተብለው የተቋቋሙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የእስራኤል መንግስት ቤተእስራእሎችን ለማዋሀድ በሚል የቀረፃቸውን ሌሎች ፕሮግራሞች የአፈፃፀማቸውን ጉዳይ መለስ ብሎ ለመገምገም አረፍ የሚልበት ታዛና የጥሞና ጊዜ ያገኛል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር፡፡

በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኙ የድሩዝ ማህበረሠብ አባላት ተለይተው ከሚታወቁበት ነገሮች አንዱ ለሚኖሩበት ሀገር መንግስት ያላቸው የማያወላውል ታማኝነት ነው፡፡ በድፍን የመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ውስጥ በሀገሬ የሚኖሩ ድሩዞች የተቃውሞ ድምፃቸውን አሠሙብኝ ወይም ደግሞ በአመጽ ተነሱብኝ ብሎ ስሞታውን ያሠማም ሆነ የሚያሠማ መንግስት ለመድሀኒትም ቢሆን ተፈልጐ አይገኝም፡፡ በ1970ና 80ዎቹ የሊባኖስ የእርስ በርስ ጦርነት ወቅት የራሳቸውን ሚሊሻ በማቋቋም ነፍጥ አንስተው ውጊያ የገጠሙት ህልውናቸዉን አደጋ ላይ ከጣሉት ታጣቂ የሚሊሻ ቡድኖች ጋር እንጂ ከሊባኖስ መንግስት ወታደሮች ጋር አልነበረም፡፡ ቤተእስራኤሎችም በእስራኤል የሚኖሩ “ድሩዞች” አይነት ነበሩ፡፡

እግራቸዉ የእስራኤልን መሬት ገና ከመርገጡ ጀምሮ የሂብሩ ጋዜጦች መብታቸውንና ነፃነታቸውን የሚጋፋ፣ ሠብአዊ ክብራቸዉንም የሚያንቋሽሽ አስከፊ የጥላቻ ዘመቻ ሲከፍቱባቸው፤ ያይጥ ምስክር ድንቢጥ እንዲሉ ጋዜጦችንም ተከትለው የተለያዩ የእስራኤል ተቋማት፣ የተለያዩ የእስራኤል የመንግስት ባለስልጣናት፣ የሀይማኖት መሪዎችና የማህበረሠብ አባላት ተዘርዝሮ የማያልቅ የዘረኝነት በደል ሲፈጽሙባቸው በእስራኤል መንግስት ላይ የነበራቸው ተስፋና እምነት እንደተጠበቀ ነበር፡፡ ቤተእስራኤሎቹ ለእስራኤል መንግስት የነበራቸውን ክብርና እምነት እንዲህ በቀላሉ እሰየው ብለው ለድርድር የሚያቀርቡት ጉዳይ ጨርሶ አልነበረም፡፡ የተስፋዋ ሀገራችን በሚሏት እስራኤል ይሆናል፤ ያጋጥመናልም ብለው ጨርሰው ባልገመቱት ሁኔታ ያ ሁሉ ግፍና በደል ወደው እስኪጠሉ ድረስ ሲፈራረቅባቸው የእስራኤል መንግስት በወቅቱ የሠጣቸዉ መልስ አልነበረም፡፡ በዘርና በቀለማቸው የተነሳም ኢትዮጵያ ውስጥ ይኖሩ በነበረበት ጊዜ እንኳ ማንም ብሏቸው ወይም ጠርቷቸው የማያውቀውን “ኩሽም” (ባሪያ) የሚል መዘባበቻ ሲሆኑ የእስራኤል መንግስት ግን ተፈልጐም እንኳ ሊገኝ አልቻለም ነበር፡፡ ይህ ሁሉ ሆኖ ግን ቤተእስራኤላውያን ከተጣዱበት የዘረኝነት መጥበሻ ላይ እንዳሉ በፀጥታ መገላበጥን እንጂ በሚያምኑትና በሚያከብሩት የእስራኤል መንግስት ላይ ልባቸውን ለማሻከርም ሆነ ፊታቸውን ለማጥቆር ጨርሶ አልሞከሩም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ በዚያን ወቅት በእስራኤል መንግስት ላይ ይህን ለማድረግ የሚያስችል አንጀት አልነበራቸውም ነበር፡፡

እንደ እስራኤል ድሩዞች ተደርገው መቆጠር ጀምረው የነበሩት ቤተእስራኤሎች ማንም ሊያደርጉት ይችላሉ ብሎ ባልገመተው ሁኔታ በእስራኤል መንግስት ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ በተቃውሞ አደባባይ በመውጣት የእየሩሳሌምንና የሌሎችም የእስራኤል ታላላቅ ከተሞች ለአንድ ወር በዘለቀ ጠንካራ የተቃውም ስብሠባና ሠልፍ ቀውጢ ያደረጉት ሀይማኖታቸውን በተመለከተ በከፍተኛ ሀፍረት ላይ የጣላቸውና በእጅጉ ያሸማቀቃቸው በደል ከደረሠባቸው በኋላ ነበር፡፡ ቤተእስራኤሎች ከዚህ በፊት በከፍተኛ ትዕግስትና ሆደ ሠፊነት ይዘዋቸው የነበሩት የተለያዩ ፈርጀ ብዙ ችግሮች ሁነኛ መፍትሄ እንዲያገኙ የእስራኤል መንግስትን ሳያሠልሱ መወትወት የጀመሩትና አልፎ አልፎም የተቃውሞ ድምፃቸውን ማሠማት የጀመሩትም ከዚህ ጊዜ በኋላ ነው፡፡ የእስራኤል መንግስት ግን የቤተእስራኤሎችን ችግር የተረዳው ገልብጦ በተቃራኒው ነበር፡፡ ለእስራኤል መንግስት የቤተእስራኤሎች ችግር እውነተኛ ችግር ሳይሆን እነሱን ለማዋሀድ በሚል የሚያደረግላቸው መጠነ ሠፊ እርዳታ ስለበዛባቸው ከመቅበጣቸው የተነሳ የመጣ ችግር አድርጐ ነበር፡፡ እናም በየጊዜው የሚያቀርቡትን የመፍትሄ አቤቱታ ለማዳመጥ የሚያስችል ጊዜውም ሆነ ልቦናና የመስሚያ ጆሮ አልነበረውም፡፡

ይልቁንስ ነገሩ ሁሉ የምግብ ፍላጐት ከመብላት ጋር ይመጣና ይጨምራል እንደሚባለው ሆኖበት ነበር፡፡ እናም አንዱ ጥፋት በጊዜ የመታረም እድል ማግኘት ሳይችል በሌላኛው ላይ እየተደራረበ ሄዶ፣ ቤተእስራኤሎቹን ከተቀረው የእስራኤል ማህበረሠብ ጋር በሚገባ ለማዋሀድ በሚል በእስራኤል መንግስት ተደግሶ የነበረውን “የቅልቅሉን” ድግስ የተጠሩት እንግዶች ሊቀምሱት እንዳይችሉ አድርጐ በአሳዛኝ ሁኔታ እንጀራውን አሻገተው፣ ወጡን እጅ እጅ እንዲል አደረገው፡፡ የእስራኤል መንግስት ቤተእስራኤሎች የራሳቸውን ቤት መግዛት እንዲችሉ ለማበረታታት በሚል በሠጣቸው ብድር አማካኝነት እስከዛሬ አስር አመት ድረስ አስር ሺ አምስት መቶ የሚሆኑ ቤተእስራኤላውያን አብዛኞቹ ባለ አንድ መኝታ ቤት የሆኑ አፓርታማዎችን ወይም የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለመግዛት ችለዋል፡፡ ከተቀሩት ውስጥ አብዛኞቹ በመንግስት የኪራይ ቤቶች ውስጥ ሲኖሩ፣ ከዛሬ አስር አመት ወዲህ ወደ እስራኤል የመጡት ደግሞ ዛሬም ድረስ በመጠለያ ጣቢያዎችና በተንቀሳቃሽ ቤቶች ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ለቤተእስራኤሎች ተዘርግቶ የነበረው የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራም እንደተገለፀው የተወሰኑትን የቤት ባለቤት ሊያደርጋቸው ቢችልም የሚፈለገውንና ቀድሞውኑ የታሠበለትን ውጤት ሳያመጣ እንደከሸፈ በእስራኤል ክኔሴት (ፓርላማ) ተመስክሮበታል፡፡ ለዚህ ደግሞ ከእስራኤል መንግስት ሌላ በተጠያቂነት ቀርቦ ቃሉን ሊሠጥ የሚችል ተጠያቂ አካል ሊኖር አይችልም፡፡ እንዴት ቢባል… የእስራኤል መንግስት ይህን የብድር ፕሮግራም የጀመርኩት ቤተእስራኤሎችን ለመርዳት በሚል “ቅን” መንፈስ ነው በማለት ሞቅ ያለ ፕሮፓጋንዳውን ቢለቅም ለፕሮግራሙ አፈፃፀም ሙሉ ቀልቡንና ልቡን ጨርሶ አልሠጠም ነበር፡፡ ፕሮግራሙን ለማስፈፀም የተጠቀመባቸው ስትራተጂዎች በሙሉ የተንጋደዱና አቅም ባላቸው ባለሙያዎች የተያዙና የተመሩ ጨርሶ አልነበሩም፡፡ የፕሮግራሙ ጠቅላላ አሠራርም የግብር ይውጣ ነበር፡፡

ይህን የብድር ፕሮግራም አሠራር በትኩረት በመከታተል አፈፃፀሙን በደንብ መገምገም የቻሉ የማህበራዊ ኑሮ ጥናት ባለሙያዎች፤ የእስራኤል መንግስት ቀድሞውን ቢሆን የእስራኤል “ኩሽም” የሆኑትን ቤተእስራኤሎች ከተቀረው “ናሽም” (ነጭ) የእስራኤል ማህበረሠብ ተለይተው በአንድ አካባቢ ብቻ ተከማችተው እንዲኖሩ ለማድረግ እጅግ በረቀቀ መንገድ ነድፎ ያዘጋጀው ፕሮግራም ነው እያሉ በሰላ ትችት ሲያብጠለጥሉት ኖረዋል፡፡ ይህን የባለሙያዎች ትችት ትክክል ነውም አይደለምም ብሎ መከራከሩ አጨቃጫቂ ሊሆን ይችላል፡፡ የሆኖ ሆኖ ግን የእስራኤል መንግስት በፈለገው አይነት አላማ ቢያዘጋጅም የመጨረሻው ውጤቱ ግን ከቀረበው ትችት ጋር አንድ አይነት ነበር፡፡ የመኖሪያ ቤት ለመግዛት ብድር የወሰዱ ቤተእስራኤሎች አብዛኞቹ ስራ አጥ ነበሩ፡፡ ስራ አላቸው የሚባሉትም ቢሆን እጅግ ዝቅተኛ ክፍያ በሚያስገኙ የስራ መስኮች ላይ የተሰማሩ ነበሩ፡፡ እናም ከወሰዱት ብድር ላይ ትንሽ ጨምረው በተሻሉና መካከለኛ ገቢ አላቸው ወደሚባሉትና ሁሉም አይነት የመሠረተ ልማት አገልግሎቶች በተሟሉባቸው አካባቢዎች ውስጥ ቤት ለመግዛት የሚችሉ አልነበሩም፡፡ ሁሉም በብድር ያገኙትን ገንዘብ ይዘው ያመሩት ርካሽ የመኖሪያ ቤቶች ወደሚሸጡባቸው፣ ምንም አይነት የመሠረተ ልማት አገልግሎቶች ባልተዘረጉባቸው ኋላቀርና ጭራሹኑ ወደተዘነጉት አካባቢዎች ነበር፡፡ ይህም ሁኔታ በድህነት የተቆራመዱ፣ በጨለማ የተዋጡና፣

ከሌላው የእስራኤል ህብረተሠብ በእጅጉ የተጉላሉ “የኩሽም ቤተእስራኤሎች” የመኖሪያ ጌቶዎች እንዲመሠረቱ ዋነኛ ምክንያት ለመሆን በቃ፡፡ የማታ ማታ አፍላ፣ ኪርያት ጋት፣ ኦር ይሁዳ፣ ኪርያት ማላኪህና የመሳሠሉት በተለያዩ የእስራኤል ከተሞች ውስጥ የሚገኙ ሠፈሮች “ናሽም” እስራኤላውያን ዝር የማይሉባቸዉ ወይም ዝር ሊሉባቸው በጣም የሚፈሯቸው የቤተእስራኤሎች መኖሪያ ጌቶ ሠፈሮች በመሆን አለም አቀፍ እውቅናን ለመጐናፀፍ ቻሉ፡፡ አሳ ሁልጊዜ በመረብ ብቻ አይጠመድም፡፡ የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራሙ እንዲህ ያለ አሳዛኝ ውጤት በማስመዝገብ ሲከሸፍ፣ ብዙዎቹ ቤተእስራኤሎችና እነሱን ለመርዳት ተብለው የተቋቋሙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የእስራኤል መንግስት ቤተእስራእሎችን ለማዋሀድ በሚል የቀረፃቸውን ሌሎች ፕሮግራሞች የአፈፃፀማቸውን ጉዳይ መለስ ብሎ ለመገምገም አረፍ የሚልበት ታዛና የጥሞና ጊዜ ያገኛል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር፡፡ ይህንን ተስፋ ያደረጉትም “አንዴ የተሸነፈ ሁለት ጊዜ ያፍራል” የሚለው እድሜ ጠገብ የማስተዋልና የብልሀት አነጋገር መቼም ቢሆን ለእስራኤል መንግስት አይጠፋውም ከሚል ግምታቸው በመነሳት ነበር፡፡ ቶማስ ሐንዴ የተባለ ደራሲ “Mr. Nicholas” በሚል ርዕስ በ1952 ዓ.ም ባሳተመው መጽሀፍ፤ አደጋን ለመጋፈጥ የማይፈልጉ ቦቅቧቃ ሰዎች፤ ምንም ቢያደርጉ ምን በአስደናቂ ነገሮች የተሞላ ህይወት ለመኖርና አስደናቂ ውጤቶችን ለመቀዳጀት ከቶውንም አይችሉም ይላል፡፡ ይህ የቶማስ ሒንዴ አባባል በቀላልና አጭር አገላለጽ ሲቀመጥ “ጀብዱ ለጀብደኞች፣ (Adventure is for fare adventurous) ማለት ነው፡፡ ከ1973 ዓ.ም የዬም ኪፑር ጦርነት ድል ማግስት ጀምሮ እስከአሁን ድረስ በወይዘሮ ጐልዳ ሜየርም ሆነ በቤንጃሚን ናታንያሁ ጠቅላይ ሚኒስትርነት የተመራው የእስራኤል መንግስት ወታደራዊ የሆነውን ነገር ለጊዜው ትተን ማህበራዊ ጉዳዮችን ብቻ በተመለከተ የወሠዳቸውን የተለያዩ የፖሊሲም ሆነ ሌሎች እርምጃዎችን በስሱ በመገምገም ብቻ የእስራኤል መንግስት ጀብዱ (Adventure) አድናቂና ጀብደኛ (Adventurous) መንግስት እንደሆነ ለመገንዘብ ምንም አይነት የአዕምሮ ብሩህነትን አይጠይቅም፡፡

አሳዛኙ ነገር ግን እነዚያ ቤተእስራኤሎችና የቤተእስራኤል ድርጅቶች ይህንን በወጉ መገንዘብ አለመቻላቸው አሊያም ጨርሰው መዘንጋታቸው ነበር፡፡ በዚህ የተነሳም የእስራኤል መንግስት፤ የመጀመሪያው ውሸት ወደ ሁለተኛው ውሸት ይመራል እንደሚባለው አይነት ከመጀመሪያው ስህተት ወደ ሁለተኛው ተሸጋገረ፡፡ የእስራኤል መንግስት ቤተእስራኤሎችን ለማዋሃድ በነደፈው ማስተር ፕላን፣ የስራ እድልን በተመለከተ ያስቀመጠው ዋነኛው ግቡ ለቤተእስራኤሎች የሙያና የክህሎት ስልጠና መስጠት የሚል ነው፡፡ በዚህ መሠረት የእስራኤል የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ለቤተእስራኤሎቹ በቂያቸው ነው ብሎ የመረጠላቸው የሙያና የክህሎት የስልጠና መስኮች የብረታብረት፣ የእንጨት ስራ፣ የነርሲንግ፣ የሆቴል መስተንግዶና፣ የልብስ ስፌት ናቸው፡፡ የእውነት ለመናገር ባለእጅነትን አምላክ ሁልጊዜ ለቤተእስራኤሎች ብሎ የጣፈው ሙያ ይመስላል፡፡ ይህ ላይ ላዩን ሲያዩት አሪፍ ነገር ይመስላል፡፡ ነገር ግን ቤተእስራኤሎች አስቀድሞ በተመረጠላቸውና በተወሰነባቸው በእነዚህ የስልጠና መስኮች የሙያ ስልጠና እንዲወስዱ ዝግጅት እየተደረገ ባለበት ወቅትም ሆነ ከዚያ ቀደም ብሎ እነዚህ የስራ መስኮች በፍልስጤማውያንና በሌሎች ዜጐች ከአፍ እስከደገፋቸው ተይዘው ነበር፡፡ እናም ቤተእስራኤሎቹ እንደታሰበው ሰልጥነው ቢወጡም፣ በእስራኤል የስራ እድል መድረክ ላይ ተወዳድረው ስራ ማግኘት በእጅጉ አዳጋች ሆነባቸው፡፡ በመጨረሻም ያተረፉት ነገር የእስራኤልን አውራጐዳናዎች ማጽዳት፣ መናኛ ስራዎችን እጅግ መናኛ በሆነ ክፍያ መስራትና የእስራኤል የአዲስ መጤዎችና የውህደት ሚኒስቴር የሁልጊዜም የእርዳታ ጥገኛ ሆኖ መቅረትን ነበር፡፡ በትምህርትና በሌሎች የማህበራዊ ዘርፎች የተገኘው ውጤትም ከዚህ ጨርሶ የተለየ አልነበረም፡፡ ቤተእስራኤላውያን በተሻለ ተዋህደውበታል ተብሎ ሊጠቀስ የሚችለው ተቋም ቢኖር የእስራኤል የጦር ሀይል ብቻ ነው፡፡

ቤተእስራኤሎች እውነተኛ እስራኤላዊ መሆናቸውንና ለእስራኤል ያላቸውን ፍቅርና ታማኝነት የህይወት መስዋዕትነትም ቢሆን በመክፈል ለማሳየት ቁርጠኛ አላማ የያዘና ለዚህም የምራቸውን የተዘጋጁ ነበሩ፡፡ የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊትን በገፍ የተቀላቀሉትም በዚህ የተነሳ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ ተቋምም ቢሆን ያጋጠማቸው የዘረኝነት መድልዎ እንዲህ በቀላሉ ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም፡፡ የእስራኤል መንግስት ችግሮቹን በጊዜ ለመፍታት ባለመቻሉ ሳይሆን ፈጽሞ ባለመፈለጉ የተነሳ በሁሉም ነገር የመጨረሻውን ዝቃጭ ደረጃ የያዘ አንድ የእስራኤል ማህበረሠብ ለመፍጠር ቻለ፡፡ ቤተእስራኤሎችም የማታ ማታ ከመላው የእስራኤል ማህበረሠብ ተለይተው የዘረኝነት ጥቃትና መድልዎ ሰለባ ሆነውና የመጨረሻውን ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ይዘው ራሳቸውን አገኙት፡፡ ይህም ሁኔታ የአብዛኞቹን ቤተእስራኤሎች ቤተሠብ ክፉኛ አመሠቃቀለው፡፡ በእድሜ የገፉት ለከፍተኛ ግራ መጋባት ሲዳረጉ፣ ወጣቶቹ ደግሞ በከፍተኛ የማንነት ቀውስ ውስጥ በመውደቃቸው “ራስታ” ለመሆን ባዘኑ፡፡ እነዚሁ ቤተእስራኤሎች በከፍተኛ የተስፋ መቁረጥ ስሜት ውስጥ ስለወደቁ፣ በወንጀል ድርጊት መሳተፍ፣ የወንጀል ቡድን አባል መሆን፣ አደንዛዥ እጽ መጠቀምና ማዘዋወር ድርጊት ውስጥ መሳተፍ ጀመሩ፡፡

በዚህም የተነሳ የቤተእስራኤል ወጣቶች የእስራኤልን እስር ቤቶች ማጨናነቅ ተያያዙት፡፡ ለህይወት ጉጉት ማጣታቸውና ከህይወት ትግል ማፈግፈጋቸውም መገዳደልንና ራስን ማጥፋትን እንደ ዋነኛ የችግር መገላገያ መፍትሄ አድርገው ይቆጥሩት ጀመር፡፡ የተቀረው የእስራኤል ህዝብ በአባታቸው ኖህ እንደተባረኩት ልጆች እንደ ሴምና ያፌት ናቸው፡፡ ማርና ወተቱን እለት ተዕለት እየተቆጣጠረ የቆዳ ስልቻቸውን የሚሞላላቸው የራሳቸው አሳላፊ አላቸው፡፡ የቤተእስራኤሎች ኩባያ ግን ባዶ ነው፡፡ ምክንያቱም ከሀገሪቱ የማርና የወተት ሠልፍ የእነሱ ተራ ከሁሉም የመጨረሻው ስለሆነ ነው፡፡ አሁን እነሱ ለአምላካቸው እያቀረቡት ያለው ፀሎት አንድ ብቻ ነው፡፡ አምላካቸው የራሳቸውን ነህምያ (ነቢይ) እንዲሠጣቸው!! አሜን ያድርግላቸው!

መልክአ፣ ኢትዮጵያ ፪

አሁንም ከአትላንታ ጆርጅያ አልወጣኹም፡፡ ባለፈው ሣምንት ጽሑፌን ለዛሬ ያቆየኹት በራቁት ዳንስ ቤት (Strip Club) ውስጥ በአግራሞት ስለተመለከትኋት ሐበሻዊ - መልክ - ራቁት - ደናሽ ልተርክላችኹ ቀጠሮ ይዤ ነበርና ከዚያው ልቀጥልላችኹ፡፡ ዓርብ እና ቅዳሜ የአሜሪካኖቹ የመዝናኛ ዕለታት ናቸው፡፡ ማታ ወጥቶ መዝናናት የሚያሰኘው ካለ ዓርብ እስኪመጣ መጠበቅ ግዴታው ነው፡፡ ከዚያ ውጭ ባሉት ቀናት ወደ ምሽት መዝናኛ ቤቶች ጐራ ማለት የብርዳም (ቁራጭ) ምሽቶች ሰለባ ያደርጋል። መዝናኛ ቤቶቹ ዐይነታቸው ለየቅል ነው። የአትላንታ ምሽት ቤቶችም እንደ ሌሎቹ የአሜሪካ ከተሞች ሁሉ ዓርብን መስለዋል። መኪና ማቆሚያዎች በተሽከርካሪዎች፣ መግቢያ በሮች ደግሞ በሰው ተጨናንቀዋል። በከተማው ይገኛሉ ሲባል ከሰማኋቸው ራቁት ዳንስ ቤቶች ሁሉ እኔ አሁን ያለሁበትን መርጫለኹ፡፡ ሐበሻዊ መልክ ያላት ደናሽ በዚህ ቤት ትገኛለችና፡፡ ቀናት በፈጀ ልመና ቦታውን ሊያስጐበኙኝ ፈቃደኛ ሆነው ያካሄዱኝ ሦስት ወንድ ጓደኞቼ ዓርብ እና ቅዳሜ ተመራጭ ቀናት መሆናቸውን በመጠቆም ይዘውኝ የወጡት በአንዱ ዓርብ ነው፡፡ ከቦታው ደረስን፡፡

ከፊት ለፊታችን በተንጣለለው የመኪና ማቆሚያ ላይ ስፍር ቁጥር የሌላቸው መኪኖች ተደርድረዋል። ዙሪያ ገባውን በተደረገ ፍለጋ እንደምንም አንድ ማቆሚያ ተገኘ፡፡ መኪናችንን ግራና ቀኙን ጠብቆ ያለምንም ስሕተት ለማቆም የሁሉም ሰው ርዳታ አስፈልጐ ነበር፡፡ ቀድመው ቦታ ይዘው በቆሙት መኪኖች ላይ ጭረት ማሳረፍ በቀላሉ የሚታለፍ ጥፋት አይደለም፡፡ በፊልም እና በማስታወቂያ የማውቃቸው የዓለም ውድ ሞዴል መኪኖች በመኪና ማቆሚያው ከተደረደሩት መካከል ቀላል የማይባለውን ቁጥር ይዘዋል፡፡ የቤቱ መለዮ የኾነው ማስታወቂያ ከሩቅ ይጣራል፡፡ በዐሥራ አምስት ደረጃዎች ከፍታ በተሠራ የቪላ ቤት ቅርጽ ግዙፍ ቤት አናት ላይ “Pink Pony” የሚል ማስታወቂያ ተለጥፎበታል፡፡ በታላላቅ ፊደላት የተቀረጸ ሲሆን ሮዝ መልክ ባለው መብራት ያሸበረቀ ነው፡፡ በሁለቱ ቃላት መካከል ፊቷን ያዞረች ራቁት ደናሽ ሴት ምስል ተጣምሮ ተሰቅሏል። ወደ መግቢያው ስንጠጋ ሁለት ሙሉ ጥቁር የፖሊስ ልብስ የለበሱ ነጭ ጠባቂዎች ዙሪያቸውን መሣሪያ ታጥቀው ወደ ዳንስ ቤቱ የሚገቡት ሰዎች ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች አለመሆኑን መታወቂያ እያገላበጡ በማየት የይለፍ ምልክት ይሰጣሉ። ተራችንን ጠብቀን የይለፍ ማኅተሙን እጃችን ላይ ካስመታን በኋላ ተራ በተራ ፍተሻችንን እያጠናቀቅን የመግቢያ ክፍያ ወደሚከፈልበት ቦታ ሄድን፡፡

ለአንድ ሰው መግቢያ 15 ዶላር ይከፈል ነበርና ለአራታችን ለመክፈል ወደ ሒሳብ ተቀባዩዋ ስንጠጋ፣ ወደኋላ ቀርቶ የነበረው ታክሲ አሽከርካሪ ጓደኛችን ለሒሳብ ተቀባዩዋ የሆነ ምልክት አሳያት፤ የገባት አልመሰለኝም፤ ምን እንደሚል ደግማ ጠየቀችው፡፡ ባለታክሲ መሆኑንና ደንበኞችን ይዞ መምጣቱን ጠቆማት፡፡ “ገባኝ” በሚል ስሜት እየተፍለቀለቀች የኛን ወስዳ የሱን መለሰችልን፡፡ ኢትዮጵያውያን ባለታክሲዎች ደንበኛ ይዘው ወደዚህ ቤት ከመጡ መግቢያ ሳይከፍሉ ገብተው ይታደማሉ ወይም ደግሞ ኮሚሽን ይቀበላሉ፡፡ በአሜሪካ ከአምስት ኢትዮጵያውያን ጋር የመገናኘት ዕድል ቢገጥማችሁ አንዱ ባለታክሲ መሆኑ ግድ ነውና እዚህ ቤትም አብረውኝ ከመጡት ጓደኞቼ አንዱ ባለታክሲ ነው፡፡ እንዲህ ላለው የከተማ ወሬ ከእነሱ የቀረበ ስለማይኖር ጥያቄዬን ለሱው መወርወር ጀመርኹ፡፡ “የዳንስ ቤቱ ጠባቂዎች ይህን ሁሉ ሽጉጥ የታጠቁት ለምንድነው?” ስል ጠየቅኹት፡፡ “የትኞቹ? በር ላይ ያለፍናቸው ነው? ፖሊሶች ናቸዋ” አለኝ፡፡ እንደገና ወደኋላ ተመልሼ መታወቂያቸውን መጠየቅ አማረኝ። በራቁት ዳንስ ቤት መግቢያ በር ላይ ፖሊሶች ቆመው በትጋት ይቆጣጠራሉ። “ለዐቅመ አዳምና ሔዋን የደረሳችሁ እንደፍጥራጥራችሁ” በሚል ስሜት ወደ ውስጥ ያሳልፋሉ፡፡ የቆረጥነውን ትኬት ሁለተኛው በር ላይ ላገኘነው ተቆጣጣሪ ሰጥተን ወደ ውስጥ ዘለቅን፡፡ በሩ ወለል ብሎ ሲከፈት ድፍረቴ ጥሎኝ ጠፋ፡፡ ሰውነቴ በላብ ተዘፈቀ፡፡ ከወደፊት ይልቅ ወደኋላ የመመለስ ፍላጐቴ ጨመረ፡፡ የደም ግፊት እንዳለበት ሰው የጭንቅላቴን የኋለኛ ክፍል ጨምድዶ ያዘኝ። በድንጋጤ ክው ብዬ ቀረኹ፡፡ ወድጄ እና ፈቅጄ የመጣሁ ሳይሆን የሆነ ሰው በሲዖል ደጃፍ አምጥቶ የጣለኝ መሰለኝ፡፡

ዐይኔ ለጊዜው ማስተዋል የቻለው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ እጅግ ሰፊ በሆነው ዳንስ ቤት ውስጥ ርቃናቸውን የሆኑ በርካታ ሴቶች ይርመሰመሳሉ፡፡ ከዚህ ቀደም አዲስ አበባ ውስጥ በጐበኘኋቸው “ስም ያወጡ” ራቁት ዳንስ ቤቶች ውስጥ የተመለከትኋቸው ኢትዮጵያውያን እንስቶች “በስንት ጣዕማቸው?” አሰኘኝ፡፡ ጡታቸውን እና ሃፍረተ -ገላቸውን በእራፊ ጨርቅም ቢሆን ሸፈን ያደርጉታል፡፡ ያኔ ይህን ቢዝነስ ሠለጠኑ ከተባሉት አገሮች ቀድተው አዲስ አበባ ያመጡትን የዳንስ ቤት ባለቤቶች ረግሜያቸው ነበር፡፡ ዛሬ ግን ለእራፊ ጨርቃቸውም ቢሆን አመሰገንኋቸው፡፡ ያጋነንኹ ካልመሰላችሁ እውነቱን ልንገራችኹ፡፡ ከቆምኹበት ብንቀሳቀስ የምወድቅ ስለመሰለኝ አንገቴን ወደ መሬት ቀብሬ ትንሽ ትንፋሽ ወሰድኹ፡፡ ጐትቼ ያመጣኋቸው ወዳጆቼ ወኔ ሲከዳኝ ሲያዩኝ ተሣሣቁብኝ፡፡ ከፊል እርቃኗን የኾነች አስተናጋጅ ፊቷን እንደ ጸዳል አብርታ በሚያብረቀርቅ ፈገግታ “ቁጥራችሁን ንገሩኝና ቦታ ልስጣችሁ?” ስትል ጠየቀች። ባይሆን ከለል ያለ ቦታ እንዳለ ለማየት እንደምንም ተጣጥሬ ቀና አልኹ፡፡ የቤቱ ስፋት በአንድ ጊዜ ይህን ለመቃኘት አያስችልም፡፡ ቀና ማለቴ ከፈራኋቸው ራቁት ሰውነቶች ጋር መልሶ አገጣጠመኝ፡፡ “የቱ ጋር እንቀመጥ?” በሚል ጠያቂ አስተያየት ሁሉም ወደ እኔ ተመለከቱ “ያስመጣሽን አንቺ ነሽ፤ እንግዲህ ተወጪው ይመስልባቸዋል፡፡ ከለል ያለ ቦታ ካገኘን ብዬ ከእነድንጋጤዬ ጠየቅኋቸው፡፡

ባለታክሲው ወዳጄ “ለዚች ልብሽ ነው እንዴ?” ሲል በድንጋጤዬ ላይ አላገጠብኝ፡፡ በቤተኝነት ስሜትም ከቤቱ መግቢያ በር በስተቀኝ በኩል ካለው የመጠጥ መሸጫ ክብ ባንኮኒ ላይ እንድንቀመጥ ወደዚያው ወሰደን፡፡ በዙሪያ ገባው ምን እየተከናወነ እንደሆነ የማየት አቅም ለጊዜው ስላጣሁ ዐይኔን በክቡ ባንኮኒ ውስጥ ቆመው መጠጥ በሚሸጡት ሴት እና ወንዶች ላይ ተከልኹ፡፡ አማራጭ ማጣት ኾኖብኝ እንጂ እኒህም የሚታዩ ሆነው አልነበረም፡፡ አንዳንዶቹ በውስጥ ሱሪ እና በጡት ማስያዣያ፣ ከፊሎቹ አጭር ቁምጣ በተጣበቀ አላባሽ፣ ከሰውነታቸው ከፊሉን አራቁተው ለማሻሻጫነት የቆሙ ናቸው፡፡ የአዲስ አበቦቹን “ከፊል ራቁት ደናሾች” ከእራፊው ጨርቅ በመለስ ያለውን ገላቸውን አጋልጠው ለሽያጭ በማቅረብ በቀጫጭን ብረቶች ታግዘው፣ ሰውነታቸውን ከወሲብ ቀስቃሽ ሙዚቃ ጋር አዋሕደው እየተገለባበጡ የሽልማት ገንዘብ ሲሰበስቡ ሳይ “አይ ድህነት አያደርገው የለ” ስል ለእንስቶቹ ሆዴ ተላውሶላቸው ነበር፡፡ በርካቶች ሥራ ፍለጋ በሚሰደዱባት የዓለም ቁንጮ በሆነችው ሀገረ አሜሪካ፣ ገላቸውን ለሽያጭ ላቀረቡት ወጣት እንስቶችስ “አይ የእንጀራ ነገር” ስል ደረቴን ልድቃላቸው ይሆን? ጉዳዩ የእንጀራ አይመስልም፤ እናም ደረት የመድቃቱ ነገር አስፈላጊ አልመሰለኝም፡፡ ቀስ እያልኹ የቤቱን መብራት እና ድምፅ ተላመድኹት፡፡ አቀማመጤን አስተካክዬም ሰረቅ እያደረግሁ ቀረብ ካሉት “የገላ ነጋዴዎች” ቅኝቴን ጀመርኹ። የቤቱ አጠቃላይ ስፋት በግምት ሁለት ሺሕ ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ እጅግ ሰፊ ወጥ አዳራሽ ነው፤ ግን ደግሞ በተለያየ መንገድ ተከፋፍሏል፡፡ አራት መዓዝን ቅርጽ ያላቸው ሰፋፊ የመጠጥ መሸጫ ባንኮኒዎች፣ በርካታ የመደነሻ መድረኮች አሉት፡፡

ነጭ እና ጥቁር ቀለም ያላቸው ሴቶች ተራ በተራ ወደ መድረኩ እየመጡ የዕርቃን ትርኢት ያሳያሉ፤ ጨርሰው ሲወርዱም ግብዣ ያቀረበላቸውን ሰው ይዘው በአንደኛው የቤቱ ኮርነር በርከት ብለው ወደተደረደሩትና የመኝታ ያህል ተለጥጠው የሶፋ መቀመጫዎች ይዘው እየሄዱ ሥራቸውን በግል ይቀጥላሉ። ልዩ ክፍያ የሚከፍል ደግሞ ሴቶቹን ወደውስጠኛው ክፍል ይዞ እንዲገባ ይፈቀድለታል፡፡ “እዚህ ቤት ግን በርግጥ ኢትዮጵያውያን ይመጣሉ?” - ቀደም ሲል የሰማሁትን መረጃ ተጠራጥሬ እንደገና ለማረጋገጥ ለባለታክሲው ያቀረብኹለት ጥያቄ ነው፡፡ በርግጥ ጥያቄው የሞኝ ይመስላል፡፡ በአዲስ አበባዎቹ የምሽት ዳንስ ቤቶች ውስጥ ተገኝተው በአዳጊ እንስቶች የውስጥ ሱሪ ገንዘብ እየጨመሩ የሚዝናኑ ኢትዮጵያውያንን በኢትዮጵያ ምድር አይቼ እንዲህ በዘመነች አገር የኢትዮጵያ ልጆች ታዳሚ መሆናቸውን መጠየቅ በርግጥ “ሞኝነት” ነው፡፡ ግን ደግሞ የቤቱን አስነዋሪነት ስመለከት በዚህ ቦታ የሀገሬ ልጆች ተሳታፊም ታዳሚም ናቸው መባሉን አምኖ መቀበል ከባድ ኾነብኝ፡፡ መብሰክሰኬ ብዙም ሳይቆይ ከጓደኞቼ የአሻግረሽ ተመልከቺ የቀስታ ጥቆማ ደረሰኝ። በቀላሉ አልታይ አለኝ፡፡ ከተቀመጥኹበት ረጅሙ የባንኮኒ ወንበር ተንጠራርቼ ዐይኔን አሻገርኹ፡፡ ከፍ ካሉት የመደነሻ መድረኮች ዝቅ ብለው ከተደረደሩት መቀመጫዎች ላይ አንዲት ሴት እና ሁለት ወንዶች ተቀምጠው እንቅስቃሴውን ፈዘው ያስተውላሉ፡፡ በመጠጥ ጭምር እየተዝናኑም ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ያየኋቸው ከርቀት ቢሆንም ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን መለየት አላስቸገረኝም፡፡ ባያውቁኝ ባላውቃቸውም እዚያ ቦታ ቁጭ ብዬ በሌላ የሀገሬ ሰው በመታየቴ ብቻ ሃፍረት ተሰምቶኝ ለመደበቅ ሞከርኹ፡፡ እነርሱ እኔ የተሰማኝ ስሜት የተሰማቸው አልመሰለኝም፡፡ ማንም በዚያ ቦታ ቢኖር ግድ ያላቸው አይመስሉም፡፡ እንደ ውጭ አገር ዜጐቹ ሁሉ እነርሱም ተራ በተራ እየተነሡ ዶላር ይሸልማሉ፡፡

በቃል ያልተመለሰው ጥያቄዬ በተግባር ተመለሰልኝ፡፡ ኢትዮጵያውያኑ በዚያ ቤት ነበሩ፡፡ ባለታክሲው ወዳጄም፤ “የኛ አገር ልጆች በብዛት የዚህ ቤት ደንበኛ አይደሉም። አልፎ አልፎ የእኔ ቢጤ ባለታክሲ ደንበኛ ይዞ ይመጣል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ እንዲህ እንዳንቺ እንግዳ እና አዲስ ሰው ከሀገር ቤት ሲመጣ አሳዩኝ ይልና ለማየት ይመጣል፡፡ ግን ከአንድ ቀን በላይ እዚህ ቤት የሚመጣ ኢትዮጵያዊ በጣም ጥቂት ነው፡፡ አንዳንዱ እዚህ በመምጣቱ ብቻ ራሱን እንደረከሰ ሰው ቆጥሮ ቤተ ክርስቲያን ሄዶ ጠበል ይጠመቃል አትላንታ ካለው ኢትዮጵያዊ በጣም ጥቂት ቁጥር የሚይዙ ሰዎች ግን የቤቱ ደንበኞች ናቸው፡፡እንዲህ ያለ ቤት ስለመኖሩ የማያውቁ ደግሞ በርካቶች ናቸው፤” አለኝ። የቤቱን ታዳሚዎች ኹኔታ በግምታዊ አኅዝ ለማስቀመጥ 300 በሚሆኑ እንግዶች መካከል ከ70 በላይ የሚሆኑ እርቃን ሴቶች ይርመሰመሳሉ፡፡ ከእኔ ጥያቄ እና ከባለታክሲው ወዳጄ መልስ ውጪ በመካከላችን ጸጥታ ሰፍኗል፡፡ ሁለቱ አገጫቸውን እጃቸው ላይ አስደግፈው ጸጥ ብለዋል፤ ተፋፍረዋልም፡፡ እውነት ነው፤ እንዲህ ያለውን ነገር አንድ ላይ ኾኖ መመልከት በራሱ ያስተፋፍራል፡፡ በቤቱ እንደምትሠራ የተነገረኝ አበሻዊ መልክ ያላት ደናሽ አለመምጣት ካሰለቸኝ ከአንድ ሰዓት በኋላ “መጣችልሽ፣ መጣችልሽ!” አለኝ ባለታክሲው ወዳጄ፡፡ ክንፍ ያለኝ ይመስል አኮበኮብኹ፤ ልጅቱን ፍለጋ አንገቴን አንቀዠቀዠኹት፡፡ መካከል ላይ ወዳለው መድረክ የምታመራ፣ ያማረ ተክለሰውነት ወዳላት ወጣት አሳየኝ፡፡ ወደ መድረኩ እየሄደች ስለሆነ ፊቷን ማየት አልቻልኹም፡፡ የሚታየኝ ጀርባዋ ነበር፡፡ አዲስ አበባ እንዳየኋቸው ሴቶች ከእራፊ በላይ በሆነ ጨርቅ ሰውነቷን ሸፍናለች፡፡ ጡቶቿን ሙሉ ለሙሉ የሚሸፍን ጡት ማስያዣ እና ሣሣ ያለም ቢሆን ታፋዋ ድረስ የሚሸፍን ቁምጣ መሰል ነገር ለብሳለች፡፡ ትልቅ ተረከዝ ያለው ቡትስ ጫማም ተጫምታለች፡፡ መድረኩን አስቀድማ ስትደንስበት ከነበረችው ባለነጭ ገላ ሴት ተረክባ የተከፈተላትን የሙዚቃ ምት ተከትላ፣ ቀስ እያለች ወደ መድረኩ ወጣች። ዙሪያውን ከበው የተቀመጡት ታዳሚዎች የቀደመችውን በጭብጨባ ሸኝተው እሷንም በጭብጨባ ተቀበሉ፡፡ የእኔ ዐይን እንዳፈጠጠ ነው፡፡ ጭንቅላቷ በአርተፊሻል፣ ፀጉር ቢሸፈንም መልኳ ሐበሻዊ መሆኑን ለመለየት ነጋሪ አላስፈለገኝም፡፡ በዝግታ የጀመረችውን ዳንስ እያፈጠነችው መጣች፡፡ ሰውነቷ በከፊል የተሸፈነ መሆኑን ስመለከት፣ ምናልባት አንዳች ማኅበረሰባዊ ሞራል በጥቂቱም ቢሆን ተጭኗት ሊሆን ይችላል ስል ጠረጠርኩኹ፤ ግን ደግሞ በቤቱ ውስጥ ከደናሾቹ እንደ አንዷ ኾና መድረክ ላይ ከወጣች በኋላ፣ ሰውነትን በእራፊ ጨርቅ መሸፈኑ ትርጉም አልባ ሆነብኝ፡፡ መጀመሪያውኑ ተወልቆ የተጣለ ነገር ነውና። ልጅቱ እንቅስቃሴዋን ቀጥላለች፡፡

ከመድረኩ ጀምረው ወደላይ የቤቱን አናት እንደምሰሶ ደግፈው የያዙትንና ለዚሁ አገልግሎት ተብለው የተዘጋጁትን ቀጫጭን ብረቶች እየተጠቀመች ስሜትን ለወሲብ በሚቀሰቅስ እንቅስቃሴ ለደቂቃዎች ስትናጥ ቆየች፡፡ ቀጠለችና አንዱን ብረት በአንድ እጇ እንደያዘች የአንድ እግር ጫማዋን አወለቀች፤ አስከትላም ሁለተኛውን ደገመች። በመድረኩ የጽዳት እና የዶላር ሽልማት ሰብሳቢ ሠራተኛ አማካኝነት የወለቀው ጫማ ተነሣ፡፡ ዳንሱ በባዶ እግር ቀጠለ፡፡ ቆየት ብላ የጡት ማስያዣዋን ፈታ ጥላ ከወገቧ በላይ እርቃኗን ሆነች፡፡ “ኦ! አምላኬ! የፈጣሪን ስም ጠራሁ። ሸላሚዎች ተነሡ፡፡ መጠኑ ስንት እንደሆነ መለየት ባልችልም ዶላር ይዘንብላት ገባ፡፡ ቆየት ብዬ እንደተረዳሁት ከቤቱ ደንበኞች ውስጥ ከዐሥር እስከ 100 ዶላር የሚሰጡ ባይጠፉም አብዛኛው ደንበኛ ግን ዘርዝሮ ይዞ አጠገባቸው ይቆምና በተለያየ ስልት እየስደነሰ ዶላሩ አምስት እና ዐሥር ላይ ሲደርስ ቦታው ሄዶ ይቀመጣል፡፡ በቤቱ ውስጥ ራቁት ደናሾቹ በመድረኩ ላይ እያሉ እያዩ ከማስደነስ ውጪ ቀርቦ መንካት የተከለከለ ነው፡፡ ልጅቷ ዳንሷንም እራፊ ጨርቋንም ከሰውነቷ ላይ እያነሣች መጣል ቀጥላለች፡፡ ሥሡን ቁምጣዋን አውልቃ ጥላ በውስጥ ሱሪ ብቻ ቀርታለች፡፡እየተዟዟረች ሽልማቷን ትሰበስባለች፡፡ አዲስ አበባ ላይ ደናሾቹን ባገኘሁ ጊዜ ዳንሱን ሥራ ብለው የያዙት አማራጭ ከማጣት ተነሥተው እንደሆነ አንጀት በሚበላ የችግር ታሪካቸው አዋዝተው ተርከውልኝ ነበር፡፡

በተለይ አንዲት 18 ዓመት በቅጡ የማይሞላት አዳጊ፤ “በትምህርቴ ብዙም ሳልገፋ እናት እና አባቴ ሁለት ታናናሾች ጥለውብኝ ሞተው እነሱን አስተምራለሁ፡፡ የምንኖረው በቀበሌ ቤት ውስጥ ነው፡፡ ረኀብ እና ጥማት ተራ በተራ እየተፈራረቀ ችግር የቤታችን አባል ቢሆንብኝ አንዷን ጐረቤት ተከትዬ ገላዬን ለመሸጥ ጐዳና ወጣሁ፤ ጓደኛዬ እዚህ የመቀጠር ዕድል ሲቀናት ለእኔ ደግሞ መንገዱን አሳየችኝ፤ ከመራብ ገላን መሸጥ፣ ገላን ከመሸጥ ደግሞ አሳይቶ ገንዘብ ማግኘት አይሻልም?” ስትልም ጠይቃኝ ነበር፡፡ ያን ጊዜ “መራብ ይሻላል” እንዳልላት እሷ ሥራውን የመረጠችው መራብ ባስከተለባት መዘዝ እንደሆነ ነግራኛለች። መራብ የሚያመጣውን መዘዝ ደግሞ ምን እንደሚያስታውሰን አላውቀውምና ዝም አልኋት፡፡ የጀመርሽው መንገድ የተሻለ ነው እንዳልል ደግሞ ድርጊቱ አስነውሮኛል። እናም ያኔ ከንፈሬን በሐዘኔታ መጥጬ በደንብ ዝም አልኳት፡፡ ይቺኛዋን ግን ምን ልበላት፡፡ እኔ እሷን እያየሁ ሐሳቤን ሳነሣ ስጥል፣ እርሷ ልብሷን ጥላ ጨርሳ በመጨረሻም እርቃን ገላዋን፣ መለመላዋን ቀርታለች፡፡ አሁን እኔም ኢትዮጵያዊ እንዳትሆን አጥብቄ ተመኘሁ። ይኼኔ እኮ እንዲህ ሆና የምታገኘውን ዶላር ከምትልክላቸው ቤተሰቦቿ ውስጥ አንዱ ወንድሟ እየፈነጨበት ይሆናል ስል አሰብኹ፡፡ የተቀመጡትም የቆሙትም ወንዶቹ በራቁት ገላዋ አፋቸውን ከፍተዋል፡፡ በዛ ሰዓት የሚደንሰው ራቁት ሰውነት የእርሷ ብቻ አልነበረም፡፡ በርካቶች ሥራ ያሉትን እርቃን ዳንስ ተያይዘውታል፡፡

ምን ያህል ሰዓት መድረክ ላይ እንደቆየች ለማስተዋል ባልችልም ሲበቃት ወረደች፡፡ መጨረሻዋን ለማየት በዓይኔ ተከተልኳት፡፡ እንደ ባልደረቦቿ እሷም የመድረኩን ካበቃች በኋላ የግሏን ጀመረች። ተጠርታ መሰለኝ ከወንዶች ጋር ተቀምጣ ስታያት ወደ ነበረች ወጣት ፈረንጅ ሴት ሄዳ ትደንስላት ጀመረች። የዳንሱ እንቅስቃሴ መተሻሸትንም ይጨምር ነበር፡፡ ሲላት ደግሞ ትቀመጥበታለች። ልጅቷን ከዛ በላይ ተከታትሎ መመልከት ለእኔ ሕመም ሆነብኝ፡፡ እንደምንም ብዬ ላነጋግራት ሞከርኩ፡፡ በጉዳዩ ላይ ከወዳጆቼ ጋር ተወያየሁ፡፡ ለማነጋገር ያለው አንድ አማራጭ ለዳንስ መጋበዝ ብቻ ሆኖ ተገኘ። ማነው የሚጋብዘው? ደፋር ከመካከላችን ጠፋ፡፡ እንደምንም ለትንሽ ደቂቃ ብዬ ባለታክሲውን አግባባሁት፡፡ በአንዷ አስተናጋጅ አማካይነት ጥሪ ተላለፈላት፡፡ ቆየት ብላ በውስጥ ሱሪ እና በጡት ማስያዣ መጣች፡፡ ቁርጥ ሐበሻ። እንደመጣች ባለታክሲውን እየተሻሸች መደነስ ጀመረች፡፡ ከየት እንደመጣች ለማወቅ በአማርኛ ሰላምታ ሰጠኋት። በማውቃቸው ጥቂት ትግርኛ ቋንቋ ሞከርኋት፡፡ አሁንም ዝም አለች፡፡ ባለታክሲው እየቀፈፈው መጣ፤ ሊታገሠኝ አልቻለም፡፡ ለመገፍተር የዳዳው ይመስላል። ሰላምታውን በፈረንጅ ቋንቋ አደረግሁና “የሀገሬ ልጅ መስለሽኝ ነው” አልኋት፡፡ ዳንሷን ሳታቋርጥ “የት ነው ሀገርሽ?” አለች። “ኢትዮጵያ”፣ አንገቷን በማወዛወዝ ምላሽ ሰጠችኝ፡፡ እኔ ከዛ አይደለሁም ማለቷ ነበር፡፡ “ከአሥመራ?” አሁንም አንገቷን አወዛወዘች፡፡ “መልክሽ ግን የኛን አገር ሰው ይመስላል” አልኋት፤ ዝም ብላ መወዛወዟን ቀጠለች፡፡ “ይውለቅልህ” ለባለታክሲው ጥያቄ አቀረበችለት፡፡ ያችኑ እራፊ ጨርቋን ልታወልቅ መሆኑ ነው፡፡ “አልፈልግም፤ አልፈልግም” አለና ተቻኩሎ ከኪሱ ካወጣቸው ዶላሮች መካከል አምስት ዶላር ሰጣት አሜሪካን ሀገር ባለታክሲን ከሌላው ሰው ለየት የሚያርገው በርካታ ዝርዝር ዶላሮች በኪሱ መያዙ ነው፡፡

እንደ ሌላው ሰው በየማሽኑ ላይ ካርድ ሲጭር አይውልም። “ዐሥር ዶላር ነው” ስትል አምስት ዶላር ጭማሪ ጠየቀችው፤ እንዲያቆያት በዐይኔ ብለማመነውም ፈቃደኛ አልሆነም። ዐሥር ዶላር ጨመረላትና እንድትሄድለት “አመሰግናለሁ” አላት፡፡ ምስጋናውን በፈረንጅ ቋንቋ ነበር ያቀረበላት፡፡ እሷም ዶላሩን ተቀብላው “አመሰግናለሁ” አለችው። መልሱ ግን በአማርኛ እንጂ በፈረንጅኛ አልነበረም።ሁለታችንም በድንጋጤ “እንዴ?” የሚል ቃል አወጣን፡፡ እኔማ ከተቀመጥኹበት ተነሥቼ ይዤ ላስቀራት ምንም አልቀረኝም። ፈገግ ብላ “ያቐንየለይ” ስትል ምስጋናውን በትግርኛ ጨምራልን፣ አረማመዷን አፍጥና ግራ አጋብታን ወደመጣችበት ተመለሰች፡፡ ዳንስ ቤቱን ለማየት ከመሄዴ በፊት ስለሐበሻዊ መልኳ ደናሽ የነገሩኝ ኢትዮጵያውያን ልጅቷ ኤርትራዊ ስለመሆኗ ሳይጠራጠሩ ነበር ያወሩኝ፡፡ ኤርትራውያን ባገኘሁ ጊዜም ስለዚችው ልጅ ጠይቄያቸው ኢትዮጵያዊ ስለመሆኗ ነው ያወሩኝ፡፡ አብረውኝ የመጡት ልጆችም ልጅቱ ኤርትራዊ ስለመሆኗ ቅንጣት ታክል ጥርጣሬ አልነበራቸውም፡፡ሁለቱም ከኛ ወገን አይደለችም ሲሉ፤ እዚያ እና እዚያ አሽቀንጥረው ሊጥሏት ይሞክራሉ፡፡ ዋናው ምክንያታቸው ደግሞ በድርጊቱ ማፈራቸው ነው፡፡ የልጅቷ ዜግነት የማወዛገቡ ሌላው ምክንያት ራሷ ልጅቷ መሆኗ ገባኝ። በሁለቱም ቋንቋ ትናገራለች፤ መልኳም የሐበሻ ነው፡፡ ለእኔ ግን መምጫዋ አላስጨነቀኝም፡፡ እሷ ከየትኛውም ትምጣ፤ ከሁለቱም ሀገር ቀያቸውን ጥለው የሚሰደዱ ዜጎች፤ ወይ በትምህርት፣ በፖለቲካ ጉዳይ አሊያም ሥራ ፍለጋ ነው፡፡ “እንጀራ ፍለጋ 15 ሺሕ ኪሎሜትር ተጉዞ ገላን በአደባባይ አራቁቶ ለሰፊ ሕዝብ መሸጥን ምን አመጣው?” አላናገረችኝም እንጂ ይህችንም እንደ አዲሳባዎቹ ልጠይቃት ያሰብኹት ጥያቄ ነበር፡፡

ምናልባትም “ከምራብ ብዬ” ነው ትለኝ ይሆናል፡፡ የሷ ግን እንደአዲሳባዎቹ መልስ አልባ አያደርግም፤ “ስንት እንጀራ ለመብላት ነው?” እላት ነበር፡፡ ለእኔ ሰቅጣጭ ከሆነብኝ ከዚህ ቤት ወጥተን ያመራነው ወደ ኢትዮጵያውያን ጭፈራ ቤት ነበር። መቼም “ከሺሻ እና ከዳንስ ቤት አትወጪም ወይ?” እንዳትሉኝ እኔ ያየሁት እንዳይቀርባችሁ ከሚል እሳቤ ነው!! ሌላ ሌላውንም ያየኹትን፣ የታዘብኹትን ያህል ቀስ እያልኹ አወጋችኋለሁ፡፡እናም በዚህ ጭፈራ ቤት በመጠጥ ተሟሙቀው፣ሲያሻቸው እየተሻሹ ሲላቸው እየተሳሳሙ፣ሲላቸው እየቆሙ፣ሲፈልጉ ደግሞ ተቀምጠው ሺሻቸውን እያጨሱ፤በጭሱ ደግሞ ታፍነው ልባቸው እስኪጠፋ በሀገራቸው ዘፈን እየጨፈሩ ያየኋቸው ጥንዶች እጅግ ጨዋ ሆነው ታዩኝ። የአስነዋሪ እና የአኩሪ ተግባር መለኪያው ጠፋብኝ፡፡ በአሜሪካ ቆይታዬ በአገሬ የማውቀውን የአስነዋሪ እና የአኩሪ ታሪክ መለኪያ ካጠፋብኝ ሌላው የጥቂት ኢትዮጵያውያን ተግባር አንዱ ደግሞ የግብረሰዶማውያን ነገር ነው፡፡ለአሜሪካኖቹ ሳይቀር አስጨናቂ በሆነው ግብረሰዶማዊነት ተዘፍቀው ያየኋቸውና ታሪካቸውን የሰማሁት ኢትዮጵያውያን እስካሁን አስጨንቀውኛል። ጎዳና የወጡ ኢትዮጵያውያንን ማየት እነዚህኞቹን እንደማየት አልከበደኝም፡፡ ግብረሰዶማዊነት በአሜሪካ መባባሱ እና ቀስ በቀስ በተለያዩ ግዛቶች ለጋብቻም እየተፈቀደ መሄዱ የኢትዮጵያንም ራስ ምታት ሆኗል። አንዲት እናት ለአቅመ አዳም የደረሰ ወንድ ልጇ “ማሚ ጓደኛዬን ላስተዋውቅሽ” ሲል በሰጣት ቀጠሮ ስላጋጠማት ነገር ያወጋችኝን ደግሞ እስቲ ልንገራችሁ። (ይቀጥላል)

አንዳንዴ ምን እንደማስብ ታውቃላችሁ? የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ፍፁም ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ አዲስ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግኝት የሚፈጥርልን ብናገኝ (ቻይናን ምን ይሳናታል?) በገንዘብ ባንችል እንኳን በ”ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ” ስም እንማጠናቸው ነበር… (ቻይና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ስታውቅ አይደል?)

ወዳጆቼ፤ የጥምቀት በዓል እንዴት አለፈ እባካችሁ? በሸጋ ያለፈ ይመስለኛል (እኔ ከናንተ ባላውቅም) ከሁሉም ያስደመመኝ ግን ምን መሰላችሁ? በጥምቀት ይወረወር የነበረው ሎሚ ተረት ሆኖ (እንደ ድህነት? ማለት ነው) ዘንድሮ በፕሪም ተተክቷል የሚባል ነገር ሰምቻለሁ፡፡ “ወጭ ለምኔ” ያሉ የዘመኑ ወጣቶች ደግሞ (በሬ ለምኔ እንደሚባለው) የሞባይል ነምበራቸውን ቆነጃጅቱ ደረት ላይ ሲወረውሩ እንደዋሉም የአውዳመት የወሬ ምንጮቼ ሹክ ብለውኛል፡፡ በደቡብ አፍሪካው የባለፈው ሰኞ የብሄራዊ ቡድናችን ግጥምያ እለት የተባለውን ሰምታችሁልኛል? “ውበት ሲለካ የኢትዮጵያ ሴቶች ናቸው ለካ!” የሚለውን ማለቴ ነው፡፡ (ለነገሩ ሲያንሳቸው እኮ ነው!!) ነገርዬውን ዝም ብዬ ሳስበው ግን የኢትዮጵያን እንስቶች ውበት ድንገት ያጐሉት ያለፈው የአፍሪካ ዋንጫ ሻምፒዮን ከሆነችው ዛምቢያ ጋር ገጥመው (ያውም በጐደሎ ተጫዋቾች) ድንቅ የኳስ ጥበብ ያሳዩት የብሄራዊ ቡድናችን አባላት ይመስሉኛል - (ያዳኑን እነ አዳነን ማለቴ ነው!) የሴቶቻችን ውበትማ አዲስ ክስተት አይደለማ!! እኔ የምለው ግን… በኢቴቪ ቀርቦ አስተያየቱን የሰጠ አንድ

በኢትዮጵያ እግር ኳስ ያበደ አድናቂ፤ ቡድናችንን ከእነሜሲ ጋር ሁሉ ሲያነፃፅር እንደ ነበር ሰምታችኋል? (ቢጋነንም ከጋለ ስሜት የመነጨ ነው ብለን እንለፈው) በነገራችሁ ላይ… ይሄ ህዳሴያችን ብዙ ታሪኮቻችንን እያደሰልን አይመስላችሁም! (በእድል እኮ አይደለም በትጋት እንጂ!) ከህዳሴው ጋር ያልታደሰልን ዋናው የህይወታችን ክፍል ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ያልታደለው ፖለቲካችን ብቻ!! እንኳንስ ሊታደስ ቀርቶ ጭርሱኑ ወደ ኋላ… ወደ ጥንቱ የጨለማ ዘመን (dark age) እየጐተተን፣ የዓለም መሳቂያ መሳለቂያ ሊያደርገን ዳር ዳር እያለ እኮ ነው! ፖለቲከኞችን በማሰር፣ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ጋዜጠኞች ለስደት በመዳረግና ወህኒ ቤት በመከርቸም፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ነፃ እንቅስቃሴ በማፈን፣ በሙስናና በመልካም አስተዳደር እጦት፣ በሰብአዊ መብት ጥሰት፣ ወዘተ… ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ስሟ እየተነሳ መሆኑ ፀሃይ የሞቀው አደባባይ ያወቀው እውነት ነው፡፡ በእርግጥ እንዲህ ያለውን ውንጀላ ባልወለደ አንጀታቸው የሚሰነዝሩት የኢትዮጵያ በጐ ነገር የማይዋጥላቸው እንደ ሂዩማንስ ራይት ዎች ያሉ ጨለምተኛ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እንደሆኑ ሁሌም ገዢው ፓርቲያችን ይነግረናል (እንዳንሳሳት ብሎ እኮ ነው!) ችግሩ ግን ምን መሰላችሁ? እዚሁ ከምርጫ ቦርድ ህጋዊ ሰርተፊኬት ተሰጥቷቸው የሚንቀሳቀሱትም ህጋዊ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተሟጋቹን ውንጀላ አንድም ሳያስቀሩ ይቀበሉታል፡፡

(ታዲያ ምን ተሻለ?) ምን መቀበል ብቻ… “መች ተነካና… ይታያል ገና!” ባይ ናቸው፡፡ (የገዢውን ፓርቲ ጉድ ማለታቸው እኮ ነው!) እኔ የምለው ግን… የአገር ሽማግሌዎች ቡድን መሪ የሆኑት ባለውለታችን ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅ ፓርቲዎችን የማስታረቅ በጐ ሚናቸውን እንዴት ዘነጉት? ለነገሩ በእሳቸውም አይፈረድም እኮ! (የአውሮፕላን ወጪ ገደላቸዋ!) እንዴ… በ97 የፖለቲካ ቀውስ ጊዜ ታስረው የነበሩትን የቅንጅት አመራሮች ከመንግስት ጋር ለማስማማት ከአሜሪካ ኢትዮጵያ የነበረውን ጉዞ የውሃ መንገድ አድርገውት ነበር እኮ! ያውም በገዛ ገንዘባቸው እየተመላለሱ፡፡ ግን ምናለ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚመላለሱበትን የአየር ትኬት ስፖንሰር ቢያደርጋቸው? (የአገር ጉዳይ አይደለም እንዴ?!) ለማንኛውም ግን ፕሮፌሰሩ አንዴ እንደምንም ወደ አገራቸው ጐራ ብለው ኢህአዴግንና ተቃዋሚዎቹን “አንተም ተው! አንተም ተው!” ቢሏቸው ሳይሻል አይቀርም ባይ ነኝ፡፡

(እረስቼው! ምርጫ ቦርድም ለካ ሌላው የፓርቲዎች የኩርፊያ ሰበብ ነው) እሱ እንኳን እርቅ ሳይሆን “ማጥራት” ነው የሚሻለው፡፡ አንዳንዴ ምን እንደማስብ ታውቃላችሁ? የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ፍፁም ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ አዲስ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግኝት የሚፈጥርልን ብናገኝ (ቻይናን ምን ይሳናታል?) በገንዘብ ባንችል እንኳን በ”ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ” ስም እንማጠናቸው ነበር… (ቻይና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ስታውቅ አይደል?) እንዴ… ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ከ15 አመት በኋላ በጐ እንቅስቃሴ የጀመረው እግር ኳሳችን እንኳ የእነቬንገርን ቀልብ ስቧል እየተባለ እኮ ነው፡፡ ፖለቲካችን ግን ይኸው 21 አመት ወደኋላ መምዘግዘግ ይዞላችኋል - ያውም ህዳሴያችንን ይዞ (ወይ ነዶ አሉ!) አያችሁ… ይሄ ክፉ ፖለቲካችን የጀመርኩትን የጥምቀት ወግ ሳልጨርስ እንዴት ጐትቶ ውስጡ እንደዶለኝ! (ፖለቲካችን እርግማንና ወቀሳ ምሱ ነው አሉ!) እኔ የምለው… በዘንድሮ የጥምቀት በዓል መዲናዋ እንዴት እንደፀዳችና እንደተዋበች በደንብ አስተውላችኋል? እንዴ… ከተማዋ 125ኛ ዓመት ልደቷን አንድ አመት ሙሉ ስታከብርም እኮ እንዲህ አላማረባትም! (አክብሮ መና ይሏል ይሄ ነው!) እውነቴን ነው የምላችሁ… የመዲናዋ ወጣት በዓሉን ያከበረው “ለጥምቀት ያልሆነ ከተማ…” በሚል አዲስ ምሳሌያዊ አባባል ይመስላል፡፡

(ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ እንዲሉ!) ቆይ ግን ያልፀዳና ያልተዋበ የመዲናዋ ስፍራ አለ እንዴ? (ማዘጋጃ ቤት ሲያሾፍ እንደኖረ የገባን አሁን ነው!) ለወትሮው የሽንትና የቆሻሻ ክምር የነበሩ ስፍራዎች ሁሉ ፀድተውና በተለያዩ ቀለማት ተኳኩለው “ሸገር” ተውሰን ያመጣናት ከተማ ልትመስለን ምን ቀራት? መርካቶ ሰባተኛ አካባቢ እንዴት በባንዲራና በፊኛ አሸበርቆ እንደነበር መስተዳድሩ አይቶት ይሆን? (ማን ነበር “ይደገም ቅዳሜ” ያለው…) ከምሬ ነው… መቼም አይቶት ከሆነ የመዲናዋ ልደት “በህዝብ ጥያቄ በድጋሚ ይከበራል” ማለቱ አይቀርም! እኔ ግን የልደቱን በድጋሚ መከበር ምንም ቢሆን እንደማልደግፍ ከወዲሁ አቋሜን ልገልፅ እወዳለሁ፡፡ እንደ 34ቱ ፓርቲዎችም ፒቲሽን ማሰባሰብ ከጀመርኩ አንድ ሁለት ቀናት አልፎኛል፡፡ አያችሁ… ባለፈው ተመክሮ እንደተገነዘብነው መስተዳድሩ የፓርቲና የፌሽታ ነገር አይሆንለትም፡፡ (ፍንዳታ ቢጤ ነው!) የመዲናዋን 125ኛ አመት ከአንድ አመት በላይ እኮ ነው ያከበረው፡፡ (ለመሆኑ ጊነስ ላይ ተመዘገበለት ይሆን?) እናላችሁ… ራሴ ያነሳሁትን የይደገም ጥያቄ ራሴ መቃወሜን እወቁልኝ፡፡ አንድ ጥያቄ ግን አለኝ፡፡ መስተዳድሩ የመዲናዋን ልደት ከአንድ አመት በላይ ሲያከብር (ራሱ ነው ያለን!) ምን ማስታወሻ የሚሆን ነገር ለከተማዋ ሰራላት? (ከፕሮፓጋንዳው ውጭ ማለቴ ነው!) ይኸውላችሁ… እኔ ከጥምቀቱ የወጣቶች ቡድን ምን ቁምነገር ቀሰምኩ መሰላችሁ? የመዲናዋ ወጣት ሲፈልግና ልቡ ያመነበት ጉዳይ ሲሆን እንደንብ መንጋ ነው - የያዘውን ስራ ዶግ አመድ ያደርገዋል፡፡ አድምቶ ይሰራዋል! (በኢህአዴግ ቋንቋ!) ይታያችሁ… የፅዳት ሠራዊት የለ! የህዝብ ንቅናቄ የለ! 1ለ5 አደረጃጀትማ ጭርሱኑ ትዝ ያለውም የለ!! አያችሁልኝ… ወጣት ባመነበት ጉዳይ ላይ እንዲህ አጀብ ያሰኛል - ያውም ያለ አንዳች የካድሬ ፕሮፓጋንዳና አጀብ!!

እኔማ ምን አሰብኩ መሰላችሁ? ጥምቀት ለምን ሁለቴ አይከበርም አልኩኝ (ግን ለራሴ ነው) (ከተማዋ እኮ አበባ መሰለች!) ጥምቀት እንዲህ ከሆነ ግን ለምንስ የፖለቲካ ጥምቀት፤ የዲሞክራሲ ጥምቀት፣ የልማት ጥምቀት፣ የመልካም አስተዳደር ጥምቀት፣ የጥበብ ጥምቀት፣ የፕሬስ ነፃነት ጥምቀት፣ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ጥምቀት፣ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል ጥምቀት ወዘተ… ወዘተ… አያሌ የህዳሴ ጥምቀቶችን አይኖሩንም ስልም ተመኘሁ - ሁሉም በአንድ መንፈስ ከልቡ የሚያከብረው፡፡ ባይገርማችሁ… በፕሮፓጋንዳ ያልተካበደ ህዳሴ እንዴት እንዳማረኝ አልነግራችሁም (አምሮት መብቴ መሰለኝ!) ውድ አንባቢያን፡- ፕሮፓጋንዳ ያልበዛበት ፖለቲካ የት እንደሚገኝ የምታውቁ ከሆነ ብትጠቁሙኝ ወሮታውን እከፍላለሁ፡፡ እኔ የምለው ግን… እኔ ብቻ ነኝ ወይስ እናንተም ናችሁ የፖለቲካ ህዳሴ የናፈቃችሁ? ለነገሩ ባይናፍቃችሁም አይፈረድባችሁም! (ተስፋ ቆርጣችሁ እኮ ነው!) እንዴ ፖለቲካችን “ከርሞ ጥጃ”፣ “ታጥቦ ጭቃ” ሲሆንባችሁስ? እውነቱን ልንገራችሁ አይደል… በጥንቱ አካሄድማ የፖለቲካ ህዳሴን መመኘት ባዶ ህልም ከመሆን ፈፅሞ አያልፍም፡፡ ለውጥ የምንሻ ከሆነ በብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድናችን ላይ የምናየውና የምንሰማው አይነት አዲስ አቅጣጫና አካሄድ ልንከተል ግድ ይለናል፡፡በእርግጥ በአንድ ጀንበር ስር ነቀል ለውጥ መጠበቅ ሲበዛ የዋህነት ነው፡፡ እንኳንስ በጦቢያ ፖለቲካ ቀርቶ በየትም አገር ቢሆን ሁሉም ነገር ቀስ በቀስ እያደገ ነው የሚመጣው፡፡

የአፍሪካ ተቃዋሚዎች ስልጣንም ሆነ ዲሞክራሲ ዛሬውኑ ካልተንበሸበሽን ብለው የሙጥኝ ሲሉባቸው ፈረንጆቹ ምን እንደሚሉ ታውቃላችሁ? “ዲሞክራሲ ሂደት ነው!” ይሉና ይገላገሏቸዋል፡፡ እንዴ ምን ያድርጉ ታዲያ? ለነገሩ የእኛዎቹንም እኮ እናውቃቸዋለን… ምርጫን የሞት ሽረት ጉዳይ ያደርጉት የለም እንዴ! ለዚህ እኮ ነው የሥነልቦና ትምህርት የሚያስፈልጋቸው፡፡ ከምሬ ነው… ፖለቲከኞቻችን የAttitude ለውጥ ካላመጡ ፖለቲካው መቼም አይለወጥም! እኔማ የስነልቦና ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ አሰልጣኝም (coach ወይም mentor ነገር) ይፈልጋሉ ባይ ነኝ! (ኢህአዴግንም ይጨምራል!) ፖለቲካ እኮ ብስለትም ብልህነትም ይፈልጋል፡፡ አጉል ብልጣብልጥነት ብቻውን የትም አላደረሰማ!! (ካላመናችሁኝ ኢህአዴግን ተመልከቱት!) ከችኩሉ ጥላቻ ተኮር ፖለቲካችን የምንላቀቀውም በጥሩ አሰልጣኝ ድጋፍ ይመስለኛል (የፖለቲካ ሰውነት ቢሻው ቢገኝማ ሽረት ነበር!) የሚገርማችሁ ግን በፖለቲካው ውስጥ ፀጉራቸው እስኪሸብት ኖረውበትም ዘንድሮም ቅንጣት ታህል ያልተለወጡ አያሌ ፖለቲከኞች በጦቢያ ምድር ሞልተው መትረፋቸው ነው፡፡ ልብ አድርጉ! እኔ ፈፅሞ የአገሬን ፖለቲከኞች የማንኳሰስ ድብቅ አጀንዳ የለኝም፡፡ የማንም ተላላኪም አይደለሁም! (ለምሳሌ የሻዕቢያ!) ራሳቸው ፖለቲከኞቻችን እኮ ራሳቸውን ለማንኳሰስ ማንንም አያክላቸውም!! (እዳ እኮ ነው የገባነው!) ባለፈው ሰሞን የኢንጂነር ሃይሉ ሻውል ፓርቲ የቀድሞ አመራሮች የቆየ ውዝግባቸወን እንደ አዲስ ሊጀምሩ መሆኑን ሰምቼ እንዴት እንደተቃጠልኩ አልነግራችሁም፡፡

እስቲ ይታያችሁ… ከኢህአዴግ ጋር የማይቀርላቸው “ልፍያ” ሳያንሳቸው እርስ በእርስ ፍልምያ መግጠማቸው ምን የሚሉት እዳ ነው (ወይስ የወዳጅነት ግጥምያ መሆኑ ነው!) እንዲህ ያሉት እኮ ፖለቲካም፣ ፓርቲም ወደሚለው ጉዳይ ከመግባታቸው በፊት ለራሳቸው ክብር መስጠትን የግድ መማር አለባቸው (እድሜማ አላስተማራቸውም!) ፈረንጆቹ postive attitude, self esteem ምናምን የሚለውን በደንብ በውስጣቸው ካሰረፁ በኋላ በማንኛውም ፈተናና ወከባ ተከበውም ቢሆን ፅናትና ብርታት ካላቸው ስኬት እንደሚቀዳጁም መማር፣ መሰልጠን፣ መለማመድ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የምርጫ ሰሞን ወከባን ለማስቀረት ብልሃቱ ዝግጅት ብቻ ነው! ኢህአዴግ ከችግሩ (ኃጢያቱ) ነፃ ነው እያልኩ ግን እንዳይመስላችሁ፡፡ የችግሩ እናት ማን ሆነና! በነገራችሁ ላይ ለኢህአዴግ የሚሰጠው ስልጠና ማተኮር ያለበት… ጦቢያን ለማሳደግ፣ ለማበልፀግ፣ ከድህነት ለማውጣት፣ ዲሞክራሲን ለማስፈን ወዘተ ከላይ የተቀባሁት እኔና እኔ ብቻ ነኝ የሚለው ክፉኛ የተጣባው አመለካከቱ ላይ ነው፡፡ “ፀሃዩን ንጉስ” በመቃወም ወደ ትግል የገባ ፓርቲ እንዴት ያንኑ የተቃወመውን አመለካከት ያቀነቅናል? (ታሪክ ራሱን ይደግማል አሉ!) ይሄ ሁሉ ስጋት ከምን የመጣ እንደሆነ እንድታውቁልኝ እሻለሁ! አያችሁ… እስከዛሬ ኦክስፎርድ ዲክሽነሪ Famine የሚለውን ቃል Food Shortage, scarcity, starvation ወዘተ በማለት ከፈታ በኋላ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ምሳሌ የሚጠቅሰው ጦቢያን እንደነበር እናውቃለን አይደል! አሁን ደግሞ ሳናስበው “ኋላ ቀር ፖለቲካ” ለሚለውም ቃል ዳግም አገራችን በዲክሽነሪው ላይ እንዳትጠቀስና ዳግም ሼም በሼም እንዳንሆን ክፉኛ ሰግቻለሁ፡፡

እናላችሁ… አገሬን እወዳለሁ የሚል ዜጋ ሁሉ ጦቢያን ከኋላቀር ፖለቲካ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማውጣት ከፍተኛ እርብርቦሽ ያደርግ ዘንድ ጥሪ ቀርቦለታል፡፡ እኔ የምለው ግን… ሰሞኑን በድራማ መልክ በኢቴቪ የሚተላለፈውን ማስታወቂያ አይታችሁልኛል - በሁለት ጫማ የሚገዙ እንስቶች የተሰራውን ማለቴ ነው፡፡ በስተመጨረሻ ላይ አንደኛዋ አዲስ የገዛችው ጫማ ተረከዟን እንደላጣትና እግሯን እንዳቃጠላት ለጓደኛዋ በምሬት ስትነግራት “በደንብ ሳትመርጪ ለምን ገዛሽ?” ትላታለች (ዋጋሽን አገኘሽ በሚል ስሜት!) ለካስ ነገርዬው ለሚያዝያው የአዲስ አበባና አካባቢ ምርጫ የተሰራ ማስታወቂያ ነው፡፡ እኔ እኮ የቻይና ጫማ ገዝታ የተቃጠለች ነበር የመሰለኝ፡፡ (ቀላል ተሸወድኩ!) ለነገሩ የማይሆን ፓርቲ መምረጥ ከቻይና ጫማም የበለጠ ሊያቃጥል ይችላል፡፡ (ፈጣሪ ይጠብቀን እንጂ!) በመጨረሻ በምርጫው ለሚሳተፉ ፓርቲዎች (ከ29ኙ ውጭ) ሁሉ የሚመች ነጠላ ዜማ እንዳገኘሁላቸው ሳበስራቸው ኩራት ይሰማኛል (ቃል በቃል መቅዳት ያኮራል ተብሎ የለ!) እንዲህ የሚል ነው የዜማው ግጥም፡- በቃ በቃ አልፈልግም ሌላ ላይመች ላይደላ… (ከጫማው ማስታወቂያም ጋር ይሄዳል አይደል? በምርጫው የምትሳተፉ ፓርቲዎች ይመቻችሁ!!) ,

  • ቤቶቹ ከቤተ መድኃኔዓለም እና ቤተ ዐማኑኤል አጠገብ የተሠሩ ነበሩ 
  • በልደት ክብረ በዓል የቱሪስቶች ቁጥር መቀነሱ ኅብረተሰቡን አስደንግጧል 

በቅዱስ ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም ከዐሥራ አንዱ ውቅር አብያተ መቅደስ ጋር በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ አራት ጥንታውያን ቤቶች በእሳት ቃጠሎ መውደማቸው ተገለጸ፡፡ ባለፈው እሁድ ለሰኞ አጥቢያ መንሥኤው ባልታወቀ ምክንያት በተነሣው የእሳት ቃጠሎ የወደሙት አራት ቤቶች የሣር ክዳን ያላቸው ፎቅ ቤቶች ሲኾኑ፣ የላሊበላን ጥንታዊ የቤቶች አሠራር የሚያሳዩ በመኾናቸው እየተጠገኑ እንዲጠበቁ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ ነበሩ፡፡ በቃጠሎው የወደሙት ጥንታውያኑ ቤቶች፤ ከቤተ ክርስቲያኒቱ የአብነት ትምህርቶች መካከል በቅኔና ዜማ ትምህርት መስጫነት ሲያገለግሉ እንደቆዩ ተገልጧል፡፡ ገኛ ቦታቸውም ከዐሥራ አንዱ አብያተ መቅደስ መካከል በታላቁ ቤተ መድኃኔዓለም እና በቤተ ዐማኑኤል አጠገብ ከ20 - 30 ሜትር ርቀት ላይ መኾኑ፣ የገዳሙ አስተዳደር ጽ/ቤት ለቅርሶቹ ደኅንነት ትኩረት ሰጥቶ በቂ ጥበቃና ክብካቤ እንደማያደርግ በካህናቱ እና ምእመናኑ የሚነሡበትን ስጋቶችና ተቃውሞዎች ያጠናከረ ነው ተብሏል፡፡ ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሰጡ የከተማው ነዋሪዎች እንደሚያስረዱት÷ የቃጠሎ አደጋው በደረሰበት ዕለት ሌሊት በሁለቱም አብያተ መቅደስ አካባቢ የገዳሙ ጥበቃ አባላት አልነበሩም፡፡

ከሙስና እና ብልሹ አሠራር ጋር ተያይዞ ጥያቄ የሚነሣባቸውና ላለፉት ስምንት ዓመታት በአስተዳዳሪነት የቆዩት የገዳሙ መምህርም ቃጠሎው በደረሰበት ስፍራ የተገኙት ከሁለት ቀናት በኋላ ነው፡፡ ቤቶቹ ሰው በማይኖርበትና ‹‹ኮር ዞን›› ተብሎ በዩኔስኮ በሚታወቀው ለቅርሶች የተለየ ስፍራ የሚገኙ ኾነው ሳለ የተከሠተው ይኸው አደጋ፣ ‹‹በአስተዳደሩ ላይ እየተጠናከሩ የመጡትን ተቃውሞዎች ትኩረት ለማስቀየስ የተፈጠረ›› አድርገው እንደሚወስዱት የስፍራው ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል በቅ/ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም በአንድ ጊዜ በተደረገው የ160 በመቶ የቱሪስቶች ዋጋ ጭማሪ ሳቢያ ዘንድሮ በተከበረው የልደተ ክርስቶስ (ቤዛ ኵሉ) እና ጥምቀት በዓላት ላይ የተገኙት የውጭ ቱሪስቶች ፍሰት ቀንሶ መስተዋሉን የዜናው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የቱሪዝሙ ባለድርሻ አካላት በበቂ ባልመከሩበት ኹኔታ በአንድ ወገን ውሳኔ ገቢን ከፍ ለማድረግ ብቻ ታስቦ ከጥር አንድ ቀን ጀምሮ በተፈጸመው በዚሁ ጭማሪ ብር 350 የነበረው የቱሪስት መግቢያ ብር 1000 እንዲኾን ተደርጓል፡፡ ባለፈው ዓመት የጥምቀት በዓል ብቻ ከአንድ ሺሕ በላይ የውጭ ቱሪስቶች መገኘታቸውን ያስታወሱት ምንጮቹ፣ በዚህ ዓመት ግን ለቱሪስቱ አስቀድሞ ከተገለጸለት የመግቢያ ዋጋ በተለየና በራቀ አኳኋን ጭማሪ በመደረጉ ምክንያት ቁጥሩ በግማሽ አንሶ መገኘቱን ገልጸዋል፡ ፡ በተለይም ያለቱር ኦፕሬተርስ በግላቸው ለጉብኝት የመጡ ቱሪስቶች ከስፍራው ከደረሱ በኋላ በናረው የመግቢያ ዋጋ ምክንያት ውቅር አብያተ መቅደሱን ሳይጎበኙ የተመለሱ እንዳሉ፣ ከእኒህም መካከል ላሊበላን መጎብኘት አዳጋች መኾኑን ለሚዲያዎች ሐሳብ የሰጡ እንደሚገኙበት ተነግሯል፡፡

የቱሪስት ፍሰት መቀነሱ በዋናነት የላሊበላ ውቅር አብያተ መቅደስ ያለውን የቱሪስት መስሕብነት ማእከል በማድረግ የተመሠረተውን የአስተዳደሩን የልማት እንቅስቃሴና የኅብረተሰቡን ኑሮ ይጎዳል ያሉት ምንጮቹ፣ በከተማው ነዋሪ ላይ ከፍተኛ ድንጋጤ መፍጠሩንም ለዝግጅት ክፍሉ አስረድተዋል፡፡ በልማትና በቅርስ ሀብቱ ተጠቃሚ ከመኾን አኳያ አካባቢው ‹‹ዕድለ ቢስ ነው›› የሚሉት የከተማው ነዋሪዎች፤ ከተማውን ከሌሎች ከተሞች ጋር ከሚያገናኙ መንገዶች አንሥቶ የተሟላ የሆስፒታል መገልገያ ዕቃዎችና የሕክምና ባለሞያዎች ያላገኘውና አገሪቱን በቱሪዝም ተጠቃሚ ሊያደርግ የሚችለው ላሊበላ:- ለመልካም አስተዳደር መስፈን የሚያሰማው ጩኽት ሰሚ ያጣ የቁራ ጩኸት እንዳይኾን በድጋሚ ጥያቄያቸውን ለማቅረብ መገደዳቸውን አስታውቀዋል፡፡

አንድ የአገራችን ገጣሚ ስለ አይጥ፣ ስለድመት፣ ስለውሻና ስለሰው የፃፈው ግጥም ጭብጡ በስድ ንባብ ቢታሰብ የሚከተለውን ተረት ይመስላል፡፡

አንዲት አይጥ ከዕለታት አንድ ቀን “ድመት” የሚል ግጥም ትጽፋለች አሉ፡፡ የግጥሙ ይዘት “ድመት ባይርባት ኖሮ እኔን አሳዳ አትበላኝም ነበር” የሚል ነው፡፡ አይጥ የፃፈችውን ግጥም ድመት ታገኛለች፡፡ ድመትም “አይጥ” የሚል ግጥም ትጽፋለች - እንደምላሽ መሆኑ ነው፡፡

አይጥና ድመት የፃፉትን ግጥሞች ሰው ያገኛል፡፡

ሰውየው፤ የቤቱ ባለቤት መሆኑ ነው፤ እጅግ አድርጐ ይናደዳል፡፡ ወረቀት ጽፈው በማየቱ እንጂ ስለምን እንደፃፉ አላነበበውም፡፡ ብቻ በንዴት

“አሃ! አይጥና ድመት በእኔ ላይ ግጥም መፃፍ ከጀመሩ፤ ተስማምተው ተነሱብኝ ማለት ነው። አድማ ነው! በጭለማ ወረቀት መበተን የመጥፎ ጊዜ ምልክት ነው፡፡ ትውልዱ ከፋ ማለት ነው። ስለዚህ እርምጃ መውሰድ ይገባኛል!” ሲል አሰበ፡፡ በመጨረሻም እንዲህ የሚል ውሳኔ አሳለፈ፡፡

“በቃ ሁለቱም ይቀጡ

ለዚያችም ወጥመድ ዘርጉ

ለዚችም ገመድ አምጡ!”

በትዕዛዙ መሠረት ወጥመድ ተዘረጋና አይጢት ተያዘች፡፡ ድመትም በገመድ ተጠፍራ ታሠረች። አይጥ ልትሞት ወደማጣጣሩ ደረሰች፡፡ ድመት በታሰረችበት እህል ውሃ አጥታ በረሃብ ልትሞት ተቃረበች፡፡

አይጥ ድመትን፤ “ለባለቤቱ ከምታሳብቂ፣ ልብ ካለሽ መልስ አትጽፊልኝም ነበር?” አለቻት፤ ወጥመድ ውስጥ ሆና!

ድመትም፤ ብስጭትጭት ብላ፤

“ቀጣፊ ነሽ! የፃፍኩልሺን መልስ ለጠላት አሳልፈሽ ከመስጠት አታነቢውም ነበር? በግልጽ አቋሜን ትረጂ ነበር! ከእንግዲህማ ስፈታ ቁም - ስቅልሽን ባላሳይሽ ዕውነት ድመት አደለሁም!” በማለት ትዝታለች!

አይጥ ድመት አሳብቃ በወጥመድ አስያዘችኝ ስትል፣ ድመት ደግሞ ለሷ የፃፍኩላትን ምላሽ ለጠላቴ (ለቤቱ ባለቤት) ሰጠችብኝ ትላለች፡፡ የቤቱ ባለቤት ደግሞ ስለምን እንደተፃፉም ሳያነብ ፍርድ ይሰጣል፡፡

ይህን የሆነውን ሁሉ ውሻ ቁጭ ብሎ ይታዘባል፡፡

“ወይ ግሩም! እነዚህ ፍጡሮች ሲሞቱም አይማማሩም!

ጠላት እንደሆኑ ኖረው ጠላት እንደሆኑ ሊሞቱ ነው፡፡ ጌታችንም፤

ጨካኝ ፍርደ -ገምድል ነው

በቀሉን ብቻ የሚያምን

በቋፍ በሥጋት የሚኖር

አንዱን ጥፋት ለማጥፋት፣ ሌላ ጥፋት የሚሠራ

ቁጥቋጦዎችን ለመንቀል፣ የሚጣላ ከተራራ…

ማንም ከማንም ላይሻል፣ ማንም ከማንም ላይበልጥ

አገር እንደበሬ ጠልፎ፣ ጥሎ ለመብላት መሯሯጥ

መንተፍተፍ…መተላለፍ፣ መጠላለፍ ሁሉን ማርገፍ!

ሁሉም መርገፍ!!” አለ፡፡

* * *

ከመጠላለፍ ይሰውረን፡፡ አደቡን ይስጠን፡፡ በተጠራጠርነው ሁሉ ፍርድ ከመስጠት ያድነን፡፡

እየደጋገምን የምናጠፋው ጥፋት እኛን ራሳችንን ይዞ እንዳይጠፋ መጠንቀቅ ያባት ነው! የምንገባው ቃል መፈፀሙን የሚያረጋግጥልን አንድም ታሪካችን፣ ሁለትም ለራስ መታመናችን ነው! በተግባር የምንሠራው በቃል የምናወራውን ካልመሰለ ዕቅዳችን፣ ስትራቴጂያችን ሁሉ፤ ውሃ የበላው ቤት እንደሚሆን አንርሳ! በታሪክ ያየነው ስህተት እንዳይደገም መጣጣር አዲስ ታሪክ መሥራት ነው!

“ታሪክ ራሱን ይደግማል” ፣ ይላል ታሪከኛው ሁሉ

እኔን ያሳሰበኝ ግና፡- ታሪክ በደገመ ቁጥር፤ ዋጋው እጅግ መቀጠሉ፤”ይለናል ሜይ ግሪንፊልድ፡፡ የሚያስከፍለን ዋጋ ብዙ ነው እንደ ማለት ነው፡፡

በርናርድ ሾው የተባለው ፀሐፊ “የአንዱ ሥጋ ለአንዱ መርዝ ነው፡፡ የአንዱ ዕድሜ ናፍቆት፤ የሌላው ዕድሜ መከፊያና ማዘኛ ነው! (one man’s meat is one man’s poison, one age’s longing another age’s loathing) የሚለው ይሄን ብጤውን ነው፡፡ የሚያስከፋን እየቀነሰ የሚናፍቀን የሚጨምርበትን ሁኔታ ለመፍጠር መደማመጥ፤ መግባባትና መተሳሰብ ያሻናል፡፡

ከፊል በእጅ፣ ከፊል በዲጂታል የሚከፈት ሠረገላ ቁልፍ (both manual and digital at the same time) ይዘን ለውጥ ማምጣት ከባድ ነው - ዘይትና ውሃ እንዲሉ፡፡ “ባለራዕይ-ለማኝ ዐባይ ሲገደብ የምሰጥህ ሁለት ብር አበድረኝ ይላል” እያሉ የአራዳ ልጆች እንደሚሳለቁት እንዳይሆን፤ በማንኛውም ረገድ ራስን መቻል እንደሚኖርብን ልብ እንበል፡፡ በምግብ ራሳችንን ችለን ረሀብተኛ ዲሞክራሲ ይዘን እንጓዝ ብንል የማያዋጣንን ያህል፤ በባዶ ሆድም ዲሞክራሲን አንግቦ መጓዝ ወንዝ አያሻግረንም፡፡ ጥቂት የናጠጡ ሀብታሞችና አያሌ የኔ-ብጤዎች ያሏት ሀገርም ሆነ ሰላሟን አጥታ ብዙ ሀብታሞችን ያፈራች ሀገር እንድትኖረን አይደለም ደፋ-ቀና የምንለው፡፡ እንደጥንቱ መፈክር “ጉዟችን ረጅም ትግላችን መራራ” ነው ማለትም አያዛልቀንም፡፡ ሁሌም ረጅም፣ ሁሌም መራራ መሆን የለበትምና! “ጊዜ ነው ይላል ሻጥረኛ፤ በጊዜ አሳቦ ሊተኛ!” ይለናል ፀጋዬ ገ/መድህን፡፡ “ሁሉ ነገር ሂደት ነው” በሚል መጠቅለያ ያለ ለውጥ፣ ያለ ዋስትና መራመድ አይቻልም፡፡ The change should be incremental እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ። የለውጥ አንቀሳቃሹ በአብዛኛው ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ነው፡፡ በዕውቀት የተገነባ፣ ለውጥ የገባው፣ ዛሬ ላይ የተደረሰው ብዙ ለውጥና መስዋዕትነት ታይቶ መሆኑን የተረዳ ወጣት እንጂ “Fast” በሚል ታርጋ የታሸገ የቢዝነስ ተሯሯጭ ለብ-ለብ ትውልድ ብቻ እንዳይሆን አገርና ነገር የገባው ወጣት መገንባት ያስፈልጋል፡፡ ያልፈጠርነውን፣ ያላስተማርነውን፣ በአግባቡ ያላነፅነውን ልጅ የሌለ ቅፅል ሰጥተን ብናሞካሸው ረብነት የለውም፡፡ በአናቱ ቅቤ ጣል ያለበት ሹሮ ዓይነት ካፒታሊዝም ኑሮአችን ቅቤ በቅቤ ነው እንደማያሰኝ ሁሉ፤ በእንዲህ ያለ ሥርዓት ውስጥ የሚያድግም ልጅ በአርቲፊሻል የተኳኳለ ከመሆን በቀር ኦርጅናሌ እንደማይሆን እናስተውል፡፡ “በወጉ ያላሳደገውን ልጅ የእከሌን ልጅ ይመስላል፤ ይላል” ማለት ይሄው ነው፡፡

የስፖርት ውድድርና የኪነጥበብ ዋጋ - በአየን ራንድ ፍልስፍና

ሕይወቱን የሚያፈቅር ሰው፣ ለሦስት ነገሮች ከሁሉም የላቀ ትልቅ ክብር መስጠት እንደሚገባው አየን ራንድ ስተምራለች። ከሁሉም የላቁ የተባሉት ሦስቱ እሴቶች እኚሁና፡ እውነታን አንጥሮ የሚገነዘብ የአእምሮ አስተውሎት (Reason)፣ የሕይወት አላማ (Purpose)፣ በራስ ብቃት መተማመን (selfesteem)። የኪነጥበብ ዋጋ እጅጉን  ልቅ የሆነው፤ እነዚህ እሴቶች ጎልተውና ጠርተው፣ በተጨባጭ ተቀርፀውና እውን ሆነው እንድናያቸው የሚያደርግ

ምናባዊ አለም ለመፍጠር ስለሚያስችል ነው። ሶስቱ የኪነጥበብ መሰረታዊ ባህርያትም፣ ከመሰረታዊዎቹ ሦስት እሴቶች ጋር (ከትኩረት፣ ከአላማ እና ከብቃት ጋር) የተሳሰሩ ናቸው። የኪነጥበብ ባሕርያት ከስፖርት ባሕርያት ጋር ምን ያህል እንደሚመሳሰሉ ተመልከቱ። 1. ኪነጥበብ፣ ዋና ዋና ቁም ነገሮችን ከትርኪምርኪ ለይቶና አጥርቶ ማሳየት ይችላል (selection and magnification)። ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ በአላስፈላጊ ነገሮች ላይ ሳይሆን በዋና ዋና ነገሮች ላይ እንድናተኩር ያደርጋል። ስለ ተጫዋቾች ችሎታ እንጂ ስለ ዘመዶቹ ቁጥር ወይም ስለ ጥርሱ ብዛት አናወራም። በቀጥታ የሚተላለፈው ውድድር ላይ፤ ተጫዋቾች ተቀባብለውና አብዶ ሰርተው ሲያልፉ፣ ኳስ ሲመቱና ጎል ሲያስገቡ ነው ማየት የምፈልገው? ወይስ የሜዳው የሳር ቅጠል ስፋትና ርዝመት፤ የተጨዋቹ ገምባሌ ስፌትና የክር አይነት ለ90 ደቂቃ ማየት እንፈልጋለን? ዋና ዋና ቁም ነገሮቹ ናቸው ጎልተው የሚወጡት። ከገምባሌ ስፌት ይልቅ የጎሉን አገባብ ለይቶ ያሳየናል፤ ደጋግሞም እንድናየው ያቀርብልና - አጥርቶ አጉልቶ። (selection and magnification) 2. ኪነጥበብ፤ ብቃትን በተጨባጭ ስጋና ደም አልብሶና በአርአያነት ሊጠቀስ የሚችል ጀግናን ቀርፆ ማሳየት ይችላል (concretization and model building)። ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ የሰውን ብቃት በእውን በተጨባጭ እንድናይ ያደርጋል። 3. ኪነጥበብ፤ የሩቁን አላማ በቅርበት እንድናጣጥመው የስኬት ጉዞውን አስተሳስሮ ማሳየት ይችላል (projection and recreation)። 

ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ በትልቅና በከባድ አላማ እንዲሁ፤ በእልህ አስጨራሽ ትንቅንቅና ፉክክር ላይ የተመሰረ ነው - በዙር ጨዋታና በጥሎ ማለፍ ፉክክሩ ጦዞ በፍፃሜው ለዋንጫ ሲደረስ እናይበታለን። ምርጥ የስፖርት ውድድር እና ምርጥ ድራማ (ድርሰት) በጣም ተመሳሳይ ከመሆናቸው የተነሳ፤ ይዘታቸውም ይዛመዳል።

ገፀ ባሕርያትና ተጫዋቾች ስፖርታዊ ውድድር ደማቅና ማራኪ የሚሆንልን፤ በብቃት የገነኑና ከባድ አላማ የያዙ ተፎካካሪ ተጫዋቾች የሚታዩበት ከሆነ ነው።

ድርሰትም ውብ እና መሳጭ የሚሆንልን፤ በጀግንነት የገነኑና ፈታኝ አላማ የያዙ ተቀናቃኝ ገፀባሕርያትን መቅረፅ ሲችል ነው። በግጭት እየጦዘ የሚሄድ የድርጊት ሰንሰለት (ሴራ) ምርጥ ስፖርታዊ ውድድር ቁጭ ብድግ

የሚያሰኘን፤ ተጫዋቾች በእያንዳንዷ ደቂቃ አላማቸው ላይ አነጣጥረው የሚጣጣሩበት ታሪክ ስለምናይበት ነው። አታልሎ ማለፍ፣ ጎል ማስገባት፣ ማሸነፍ፣ ዋንጫ መውሰድ... የተጫዋቾቹ ድርጊት በሙሉ፣ ፉክክሩና ጥሎ ማለፉ ሁሉ እርስ በርስ የተሳሰሩ ናቸው። በአላማ ላይ ያነጣጠረ የፍልሚያ፣ የግጭት፣ የፉክክር መርሃ ግብር የምርጥ ስፖርታዊ ውድድር መለያ ነው - በግብግብ እየጦዘ የሚሄድ የውድድር ሰንሰለት (ሴራ) ልንለው እንችላለን።

ምርጥ ድርሰት ልብ ሰቅሎ የሚያጓጓን፤ ገፀባሕርያት በእያንዳንዷ ደቂቃ አላማቸው ላይ አተኩረው ሲታገሉ፣ ሲወጡና ሲወርዱ የሚያሳይ ታሪክ ስለሚያቀርብልን ነው። መውጪያ ወይም መግቢያ ቀዳዳ መፈለግ፣ ማምለጥ ወይም ማሳደድ፣ መያዝ ወይም ነፃ መውጣት... የገፀባሕርያቱ እንቅስቃሴ በሙሉ አላማን ለስኬት ለማብቃት

የሚደረግ ነው። ሁሉም ድርጊቶች የተሳሰሩ ናቸው - በአላማ ላይ ያነጣጠረ የትንቅንቅ፣ የግጭትና

የፉክክር ታሪክ ነው - በግጭት እየጦዘ የሚሄድ የድርጊት ሰንሰለት (ሴራ)። የአቀራረብ ዘይቤ (ስታይል)

የስፖርታዊ ውድድሮች አቀራረብ በአዘጋጆቹ መንፈስና ዝንባሌ ይለያይ የለ? በድርሰትም እንደዚያው ነው። የሁለት ድርሰቶች ታሪክ ተመሳሳይ ቢሆን እንኳ እንደደራሲዎቹ መንፈስ አቀራረባቸው ሊለያይ ይችላል። የአንዱ ደራሲ የአቀራረብ መንፈስ (ስታይል) እንደ አፍሪካ ዋንጫ በወግ የደበዘዘ በጥሬ ስሜት የተንዘፈዘፈ ይሆናል። የሌላኛው

ደራሲ ስታይ ደግሞ፣ እንደ አሜሪካ የቅርጫት ኳስ ዋንጫ ያሸበረቀና የተሽቀረቀረ ይሆናል። የአንዱ

ደራሲ፤ እንደ ጀርመኑ ቡንደስ ሊጋ ቆጠብ ደደር ያለ፤ የሌላኛው እንደ እንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የተጯጯኸና የተቀወጠ። ስፖርታዊ ወድድርና ድርሰት፣ ሌላ ተመሳሳይ ተፈጥሮ አላቸው። ሁለቱም፤ በቅጡ የሚታወቅ ጭብጥ (ጥቅል ሃሳብ) ሊኖራቸው ይገባል። ጭብጥ፡ የምን ጨዋታ የምን ድርሰት? ስለተጫዋቾችም ሆነ ስለ ዋንጫ፤ ስለ ጥሎ ማለፍም ሆነ ስለ ፉክክሩ ጡዘት፣ አልያም ስለውድድሩ የአቀራረብ መንፈስ መነጋገር የምንችለው፤ በቅድሚያ የውድድሩን ምንነት ስናውቅ ነው። በአጭሩ የውድድሩ ይዘት፣ ሂደትና

አቀራርብ፤ በውድድሩ ምንነት ላይ የተመሰረተ መሆን ይገባዋል። “የ2013 የአፍሪካ እግርኳስ ዋንጫ”፣ “የ2012 ኦሊምፒክ”፣ “የ2014 የአለምአትሌቲክስ ሻምፒዮና”፣ “የሰፈር ልጆች የእግር ኳስ ግጥሚያ”፣ “የባለስልጣናትና የነጋዴዎች የእግር ኳስ ጨዋታ”... እነዚህ ሁሉ አንድ አይነት ይዘት ወይም አቀራረብ ሊኖራቸው አይችልም። የውድድሩን ጭብጥ ለይተን በጥቅሉ ስናውቅ ነው፤ ምን አይነት ተጫዋቾችና ዋንጫ፣ ምን አይነት ትንቅንቅና

የውድድር መርሃ ግብር እንደሚኖር በአጠቃላይ የውድድሩ ይዘትና ሂደት ምን መምሰል እንዳለበት

መምረጥና መወሰን የሚቻለው። የውድድሩ ይዘት፤ ሂደትና አቀራረብ፤ በውድድሩ ጭብጥ ይወሰናል

ማለት ነው። የወዳጅነት ወይም የእርዳታ ማሰባሰቢያ ውድድርንና የአለም ዋንጫንና ኦሊምፒክን በአንድ አይነት መንፈስ ማቅረብ አይቻልም፤ ውድድሮቹና ተጫዋቾቹም ይለያያሉ።

 

በድርሰትም እንዲሁ፤ ገፀባሕርያቱንና አላማቸውን፣ ግጭቱንና ሴራውን ለመምረጥና ለመወሰን፣ በቅድሚያ ደራሲው በምን ዙሪያ ለመፃፍ እንደሚፈልግ ጭብጡን ለይቶ ማወቅ ይጠበቅበታል። ለምሳሌ የዴርቶጋዳ ጭብጥ፤ “በጥንታዊ መሰረት ላይ ለኢትዮጵያ ትንሳኤ የሚባትሉ ዜጎች” የሚል ነው። “የሰዎችን ህይወት የሚያሰናክልና የሚያዋርድ ኋላቀር ህብረተሰብ ውስጥ የሚኖሩ ሚስኪን ፍቅረኞች” ... ይሄ ደግሞ የፍቅር እስከ መቃብር ጭብጥ ነው። “ድሆችን የሚበድል ፍትህ የተጓደለበት ስርዓት ውስጥ የሚኖር ጀግና” ... ዘ ሚዘረብልስ የተሰኘ መፅሃፍ። “አገርን የሚዋጅና ፍትህን የሚፈፅሙ ጀብደኞች” ... ዘ ስሪ ማስከቲርስ። “ፍቅሩንና ነፃነቱን ተቀምቶ ፈተና ውስጥ የገባ ቅን ሰው” ... ዘ ፍዩጀቲቭ የተሰኘ ፊልም። የጭብጡ ስፋትም ሆነ ጥልቀት የደራሲው ምርጫ ነው። ቅልብጭ ያለ እና የሾለ ሊሆን ይችላል። የእውቀቱንና የአቅሙን ያህል የሚመጥን፣ የዝንባሌውንና የፍላጎቱን አዝማሚያ የሚጣጣም መሆን አለበት።

ከላይ እንደተጠቀሰው፤ የድርሰት ዋና አላባዊያን 1. ጭብጥ፣ 2. የገፀባሕርያት አሳሳል (አላማን ጨምሮ)፣ 3. ሴራ (ግጭትን ጨምሮ)፣ 4. የአቀራረብ ዘይቤ (ስታይል) ናቸው። በስፖርታዊ ውድድርም ውስጥ፤ አላባዊያኑ ተመሳሳይ ናቸው። እስቲ በገፀባሕርያት አሳሳልና በሴራ ላይ በማተኮር ተመሳሳይነታቸውን በደንብ ለመመልከት እንሞክር።

የገፀ ባሕርያት አሳሳል፡

ከ31 አመት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ የተመለሰ፤ ባለፈው የአፍሪካ ዋንጫ የወሰደ፤ በማጣሪያው ያለፈ፤ በፕሮፌሽናል ተጫዋቾች የተገነባ፣ በውዝግብ የተበጠበጠ፤ በሽልማት ቃል የተገባለት፣ ብዙ ፈተና ያለበት ... የቡድን አወቃቀርና አመራር፣ የስፖርተኞች ብቃትና ዝግጅት፣ የአሰልጣኝ ብቃትና ዝግጅት ... ዋና ዋና ነገሮች ላይ ማተኮር። ለምሳሌ የፊዚክስ ሳይንቲስት፣ የአውሮፕላን ኢንጂነር፣ የአንጎል ሃኪም፣ የፋብሪካ ምርጥ ማኔጀር፣ የቢዝነስ ጥበበኛ፣ ምርጥ አልሞ ተኳሽ .... ላይ አናተኩርም። በዘመድ፣ በጓደኝነት፣ በጉቦ፣ በእጣ፣ በሃይማኖት ተከታይነት፣ በብሄረሰብ፣ ... አጓጉል ሃሳቦችን አናመጣም። በጉዳይህ ላይ ዋና ዋና ነገሮችን ለይቶ ማወቅና እነሱን በትኩረት ማስተዋል... የተዘበራረቀ፣ የተንሸዋረረ፣ የዘፈቀደ፣ የፈዘዘ፣ የደነዘዘ፣ የተደናበረ አስተሳሰብ እንዳይኖረን ያደርጋል።

የተወዳዳሪ ቡድኖች፣ የአሰልጣኞች፣ የተወዳዳሪዎች ... ማንነት፣ አላማ፣ ብቃት፣ አቅም፣ ዝንባሌ... የተወሰነ መረጃ “ከኤክስፖዚሽን” እናገኛለን። እንግዲህ የስፖርታዊ ውድድር ኤክስፖዚሽን የሚቀርበው፤ በማጣሪያ ውድድሮች ላይ፣ በዝግጅትና በልምምድ ወቅት፣ እንዲሁም በሚዲያ ዘገባዎች አማካኝነት ነው። የገፀባሕርያቱ ማንነት እየጎላ የሚመጣውና እየጠራ የሚታየን ግን... ታሪኩ ከጀመረ በኋላ ወይም በግጭት የተወጠረ የድርጊት ሰንሰለት ውስጥ (ሴራው ውስጥ) ነው። የተጨዋቾቹ ማንነትና ብቃት በግላጭ የምናየውም፤ ጨዋታው ከጀመረ በኋላ በትንቅንቅ የከረረ በውድድሩ ሂደት ውስጥ (በሴራው ሰንሰለት ውስጥ) ነው። ይሄኔ መሪውና ተቀናቃኝ ፍንትው ብለው ይወጣሉ። የገፀባሕርያቱ ልዩ መልክ ነጥሮ ይወጣል - ዋና መሪ ገፀባሕርይ፣ ዋና ተቀናቃኝ ገፀባሕርይ፣ ደጋፊ ገፀባሕርያት፣ እኩይ ገፀባሕርያት...

እንደ ጥሩ ድርሰት ሁሉ፤ ጥሩ ስፖርታዊ ውድድርም ቢያንስ ሁለት ጀግና ገፀባሕርያት (ጠንካራ ተፎካካሪዎች) ያስፈልጉታል። ነገር ግን፣ ጀግኖቹ እንደ የብቃታቸውና እንደ የዝንባሌያቸው፤ አላማቸውን ለማሳካት የሚመርጡት መንገድ ይለያያል። መጥፎ ነገር የመስራት አባዜ አልተጠናወታቸውም። ግን፤ አንዱ በፅናት ትክክለኛውን መንገድ የሚከተል፣ ሌላኛው ግን አንዳንዴ ወደ ስህተት ለመግባት የሚቃጣው ሊሆን ይችላል - ለምሳሌ ሰዓት ማባከንና ተጠለፍኩ ብሎ የውሸት መውደቅ። ቢሆንም፤ በጨዋታው ህግ እየተዳኙ የሚጫወቱ ናቸው። ሜዳ ውስጥ የገቡት፣ በሰዓት ማባከን ችሎታ ወይም ተጠለፍኩ ብሎ ዳኛ በማታለል ጥበባቸው አይደለም። የእግር ኳስ ብቃታቸውና ጥረታቸው ነው ዋናው ነገር። ዋና አላማቸውም ማታለልና ማሰናከር አይደለም። ዋና አላማቸው ተጫውቶ ማሸነፍ ነው። የተለያዩ ጉድለቶች ቢኖሯቸውም፣ በጥቅሉ ጀግኖች ናቸው። እንደየጉድለታቸው መጠንም ችግር ይገጥማቸዋል።

1. ዋናው መሪ ገፀባሕርይ (ፕሮታጎኒስት)፡ እንግዲህ በላቀ ብቃትና በጥሩ ጨዋታ እያሸነፈ ዋንጫ ለመውሰድ ቆርጦ የተነሳ ነው ዋናው መሪ ገፀባሕርይ። በምርጥ አጥቂዎች ላይ የተገነባ ቡድን ነው እንበል። (ከድርሰት አለም ውስጥ አንድ ሁለት ፕሮታጎኒስቶችን ብንጠቅስስ? ለምሳሌ የባንክ ዘራፊውን አሳድዶ ለመያዝ የሚፈልግ ፖሊስ፣ ወይም ፍቅረኛውን ከአጋቾች ለማዳን የሚፈልግ እጮኛ)

2. ዋናው ተቀናቃኝ ገፀባሕርይ (አንታጎኒስት)፡ የተወሰኑ ጉድለቶች እንዳሉት በማመን በመከላከል ላይ አተኩሮ ለማሸነፍ በእልህ የሚጫወት ቡድን ሊሆን ይችላል። (በድርሰቱ አለም ደግሞ፤ የባንክ ዘራፊውን ለመያዝ ግብረአበሮቹን ማግባባት አለብን የሚል ፖሊስ፤ አልያም ከአጋቾቹ ጋር በመደራደር ታጋቿን ለማስለቀቅ የሚጣጣር አባት...)

ተጨማሪ ገፀባህርያት

1. ደጋፊ ገፀባሕርያት፡ ዳኞች፣ አሰልጣኞች፣ ተመልካቾች፣ አድናቂዎች፣ ጋዜጠኞች፣ ሸላሚዎች...

2. እኩይ ገፀባሕርያት (ቪሌይን)፡ ተሳዳቢ ቲፎዞ፣ አድሏዊ ዳኛ፣ የሚያዛባ ጋዜጠኛ፣ የቁማር ማፊያ፣ በዘርና በአገር ተቧድኖ ውድድሩን የሚበጠብጥ ጋጠወጥ፣ ኳስ መጫወትም ሆነ ማየት የለባችሁም የሚል አክራሪ፣ ከኳስ ደስታ ይልቅ ለችግረኞች ሃዘኔታ ቅድሚያ እንስጥ የሚል ዘመነኛ ባህታዊ... ወዘተ

ጠንካራ ሴራ፡ የጀግኖች ግጭት

ሁለቱ ጀግና ገፀባሕርያት (በወኔ የታነፀው ፖሊስና ትእግስት የተላበሰው ባልደረባው) አላማቸው ተመሳሳይ ቢሆንም ተቀናቃኝ መሆናቸው አይቀርም። ሁለቱም ጀግኖች ስለሆኑም ግጭታቸው ጠንካራ ይሆናል - (የፍፃሜ ውድድር ላይ እንደሚገናኙ ተፎካካሪ ቡድኖች ማለት ነው)።

ለምሳሌ ዘ ሚዘረብልስ የተሰኘው የቪክቶር ሁጎን ድርሰት መጥቀስ ይቻላል። ዋናው ገፀባሕርይ ፍትሕ ለማግኘት የሚታትር ነው። ተቀናቃኙ ደግሞ፣ ህግ መከበር አለበት ይላል - ዣቬር። ለያዙት አላማ ፅኑ ናቸው፤ ብቃታቸውን ተጠቅመው ይፋጫሉ። ዣቬር ባይኖር የዣን ቫልዣ ታሪክ ይኮሰምናል። ጠንካራ ተፎካካሪ እንደሌለው የፍፃሜ ውድድር፤ እርባና ቢስ ታሪክ ይሆናል።

ታዲያ በሁለቱ ጀግኖች ግጭት መሃል፤ ዣን ቫልዣን እንደ አባት የምትወደው ወጣት ሴት አለች። ይህችን ሴት በመጠቀም ዣን ቫልዣን ለመዝረፍና ለመጉዳት የሚፈልጉ መናኛ እኩይ ገፀባህርያትም ይኖራሉ። ግን የዣን ቫልዣ ትንቅንቅ ከመናኛና ከእኩይ ገፀባሕርያት ጋር አይደለም። ከጠንካራውና ከጀግናው ዣቬር ጋር ነው ትግሉ። ድርሰቱ ከምዕተ አመት በኋላም እግጅ ተወዳጅ ታሪክ ለመሆን የበቃበት ትልቁ ሚስጥር ይሄው ነው።።

ከዘመኑ ፊልሞችም አንድ ምሳሌ መጥቀስ ይቻላል - ሃሪሰን ፎርድ የሚሰራበት ዘ ፊጁቲቭ የተሰኘው ፊልም። ሚስትህን ገድለሃል ተብሎ በሃሰት የተፈረደበት ሃኪም ከእስር ሲያመልጥ ነው ታሪኩ የሚጀምረው። ሚስቱን የገደሉበትና በተንኮል ለእስር የዳረጉትን ሰዎች አጋልጦ ንፁህነቱን ሳያስመሰክር ወደ እስር መመለስ አይፈልግም። ይህን አላማ ማሳካት አለበት። ኮምጫጫው ህግ አስከባሪ ደግሞ፤ ከእስር ያመለጡ ሰዎችን የገቡበት ገብቶ መያዝና ማሰር ስራው ነው። ህግ መከበር አለበት ባይ ነው። የሁለቱም አላማ ትክክል ነው፤ ፅናት አላቸው። አላማቸውን የሚያሳኩበት ብቃትና ብርታት አላቸው። ፍጭቱ ሃይለኛ ነው። ፊልሙ ደግሞ እጅግ መሳጭ ታሪክ።

መናኛዎቹ እኩይ ገፀባሕርያት፣ በራሳቸው አቅም የታሪኩን አቅጣጫ የመቀየር አቅም የላቸው - ጀግኖቹ ገፀባሕርያት ደካማ ካልሆኑና ካልፈቀዱላቸው በቀር። የጀግኖቹ ግጭት ተባብሶና ጦዞ እልባት ላይ ሲደርስ፤ እኩዮቹ ገፀባሕርያት እርቃናቸውን ይቀራሉ። በእግር ኳስ ውድድርም ተመሳሳይ ነው። ጨዋታው የሚያምረው፣ ከፍተኛ ብቃት ባላቸው ምርጥ ተጫዋቾች ሲወዳደሩ ነው።

ሦስቱ የኪነጥበብ ባሕርያት ሲጓደሉ

ዋና ዋና ነገሮች ላይ አለማተኮር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ለመገንዘብ ምሳሌዎችን ልጥቀስላችሁ። ያህል ይሉሃል ይሄ ነው። የተፈነከተ ተመልካች ላይ የሚደረግ የረቀቀ ህክምና ስናይ ብንውል? አጥቂው እያታለለ ሲያልፍ ለአፍታ አሳይቶ ከዚያ በኋላ ለ10 ደቂቃ ያህል የሜዳውን የሳር ቅጠል ብዛትና ስፋት ከተለያየ አቅጣጫ እየቀረፀ ቢያሳየንስ? አንድ ሁለት ተቀባብለው፣ ወደ ግራ ክንፍ አሻግረው፣ ወደ ግብ... ካሜራው ይህንን አቋርጦ ጨዋታው እስኪያልቅ ድረስ የተጨዋቹ የገምባሌ ስፌት እና የፀጉሩ ቀለም ከተለያየ አቅጣጫ እየደጋገመ ቢያሳየንስ? በቲቪ በቀጥታ የሚተላለፈው ጨዋታው ሳይሆን፤ የአሰልጣኞችን ክርክርና ዛቻ ወይም የተጫዋቾችን ተረብና የቅፅል ስም አጠራር ቢሆንስ? ወይም፤ በትንታኔና በቲዎሪ ፉክክር ብቻ ነገሩ ቢጠናቀቅስ? ተጨባጭ ታሪክ ሳይኖረው፤ በገለፃና በትንታኔ የታጨቀ ድርሰትም፤ ከሬድዮ ቶክ ሾው የተሻለ ዋጋ አይኖረውም።

ብቃት የማያስፈልገው ውድድር ቢሆንና ማጣሪያና ምርጫ ባይኖርስ? ለምሳሌ በእጣ ሊሆን ይችላል። እግር ኳስ ማየት፤ የሎተሪ እጣ ሲወጣ ከማየት የተለየ አይሆንም ነበር። የተጫዋቾችን ብቃት መመዘን ባንችል ኖሮስ? ስለ ቼዝ የማናውቅ ከሆነ የቼዝ ጨዋታ ለማየት እንጓጓም። ምክንያቱም የተጨዋቾችን ብቃት መመዘን አንችልም። ማሸነፍና ዋንጫ ማግኘት የሚቻለው በእርዳታ ቢሆንስ ኖሮ? አንዱ ቡድን በባዶ እግር በአምስት ሰው ብቻ እንዲጫወት የሚፈረድበት ቢሆን?ተጫዋቾች በብቃታቸው የማይመረጡ ቢሆንስ? ስማቸው በ”ኤ” የሚጀምርና በውድቅት ሌሊት የተወለዱ ብቻ የሚካፈሉበት ውድድር ቢሆንስ? ብቃትን አጉልቶ የማያወጣ ውድድር፤ ከንቱ ልፊያ ይሆናል። ይህ ነው የሚባል ብቃት በሌላቸው ገፀባሕርያት የታጨቀ ድርሰትም እንደዚያው ነው።

ግብ እና ዋንጫ ባይኖርስ? (7 ቁጥሩ ለ9 አሳለፈ፣ ጠለዘ፣ ነዳ ... ይህንን ለስንት ደቂቃ ሳይሰለቸን ማየት እንችላለን? አሸናፊው ተለይቶ የሚታወቀው በቲፎዞ ብዛት ቢሆንስ? ጎል ሲያገባ እንደ ዳኛው ፍላጎት፣ ለሌኛው ቡድን ነጥብ ቢሰጥስ? ለማሸነፍ ባይጫወቱስ? በይሉኝታ መሸነፍ፣ ለሌላው አዝኖ ራስን መስዋዕት ማድረግ፣ ያሸነፈ ቡድን ራስ ወዳድ ተብሎ ቢወገዝስ? የዘንድሮው ሻምፒዮና፣ በስህተት በራሱ ላይ ብዙ ግብ ያስቆጠረ ቡድን ነው ቢባልስ?

  • •ውሳኔውን የተቃወሙት የቅ/ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ የመልቀቂያ ደብዳቤ አስገብተዋል
  •  የሰላሙና የዕርቅ ሂደቱ ‹‹ኹኔታዎች ሲመቻቹ›› በሌላ አደራዳሪ አካል ይቀጥላል
  •  ‹‹6ውን ፓትርያሪክ በአንድነት ለ መምረጥ የተደረገው ጥረት አል ተሳካም›› የቅ/ሲኖዶሱ መግለጫ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ የስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ ሂደት ሕገ ቤተ ክርስቲያንንና ቀኖናውን ጠብቆ እንዲቀጥል ወሰነ፡፡ ቅ/ሲኖዶሱ ከዚህ ውሳኔ ላይ የደረሰው ከጥር 6 - 8 ቀን 2005 ዓ.ም በወቅታዊ የቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳይ ላይ ሲያካሂድ የቆየውን የምልአተ ጉባኤ አስቸኳይ ስብሰባ ሲያጠናቀቅ ባወጣው ባለሦስት ነጥብ የውሳኔ መግለጫው ነው፡፡

ከአምስተኛው ፓትርያሪክ ኅልፈተ ሕይወት በኋላ በሰሜን አሜሪካ ከሚገኙ አባቶች ጋር ተጀምሮ ለቆየው የሰላምና አንድነት ጉባኤ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ ልኡካኑን በመላክ፣ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ፣ ሊያቀራርቡ የሚችሉ በርካታ የሰላም አማራጮችን ማቅረቡን በመግለጫው ያስታወሰው ቅ/ሲኖዶሱ፤ ‹‹በዚያ በኩል ባሉ አባቶች ምንም ዐይነት የሰላም ፍንጭ አለመታየቱንና የሰላም ስምምነት ለመፈጸም አለመቻሉን›› ገልጿል፡፡ በአሁኑ ወቅት በመንበረ ፕትርክናው ከሚታየው ክፍተት አኳያ ቤተ ክርስቲያን ያለመሪ ለብዙ ጊዜ እንድትቆይ ማድረግ÷ ‹‹መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሥራዋ እንዲስተጓጎል፣ መልካም አስተዳደሯ እንዲዳከም፣ ዕድገቷም እንዲቀጨጭ የሚያደርግ በመኾኑ›› ለስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ የተጀመረው ዝግጅት እንዲቀጥል መወሰኑን ቅ/ሲኖዶሱ አስታውቋል፡፡

ቅ/ሲኖዶሱ አሜሪካ ድረስ አራት ጊዜ ልኡካኑን መላኩን፣ በሰላም ፈላጊነቱም ‹‹ኑ እና አብረን እንሥራ፣ አብረን እንምረጥ›› ከማለት ውጪ ሌላ የሚጠበቅበት ሓላፊነት ሊኖር እንደማይችል በመግለጫው አመልክቷል፡ ፡ የስድስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ ከመከናወኑ በፊት የሰላምና አንድነት ጉባኤው ተካሂዶ ከቀድሞው አራተኛ ፓትርያሪክ ጋር በሰሜን አሜሪካ ያሉት አባቶች ወደ አገራቸውና ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲገቡ፣ የመምረጥና የመመረጥ መብታቸው እንደሚጠበቅላቸው፣ በዚህም ስምምነቱ እንዲፈጸምና ነገሩ እንዲቋጭ በሚገባ ቢያስረዳም የተጠበቀው ስምምነት ሳይፈጸም መቅረቱን በመግለጫው አትቷል፡፡ ይህንንም ቅ/ሲኖዶሱ እጅግ አሳዛኝ ኾኖ እንዳገኘው ገልጿል፡፡

በመሪ አለመኖር ምክንያት የቤተ ክርስቲያን ሥራ በእጅጉ እየተጎዳ እያየ ተጨማሪ ጊዜ መስጠት ቤተ ክርስቲያንን ለከፍተኛ ውድቀት የሚዳርግ፣ በእግዚአብሔርና በታሪክ ፊት ወቀሳን የሚያስከትል መኾኑን በመገንዘብ ቀደም ሲል አስመራጭ ኮሚቴ መሠየሙን ያስታወሰው የቅ/ሲኖዶሱ መግለጫ፣ የምርጫውም ሂደት ‹‹በእግዚአብሔር ቸርነትና በምእመናን ድጋፍ ሕገ ቤተ ክርስቲያንና ቀኖናው ተጠብቆ እንደሚከናወን ፍጹም ጥርጥር የለንም›› ብሏል፡ ፡ የፓትርያሪክ ምርጫ ጊዜው በቁርጥ ባይታወቅም እስከ ጥር መጨረሻ ድረስ ዕጩ እንዲያቀርብ የተሠየመው የአስመራጭ ኮሚቴው ሂደት እንደሚወስነው ከመግለጫው በኋላ ለጋዜጠኞች ጥያቄዎች ምላሽ በሰጡ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከፍተኛ ሓላፊዎች ተገልጿል፡፡

ውጥረት ሰፍኖበት እንደነበር በተገለጸው የምልአተ ጉባኤው ስብሰባ÷ ‹‹የዕርቀ ሰላሙን ፍጻሜ በጊዜ ገደብ ጠብቀን በውጭ ከሚገኙት አባቶች ጋር ምርጫውን በአንድነት እናካሂድ›› የሚሉ ሊቃነ ጳጳሳት በውሳኔ መልክ የወጣውን የቅ/ሲኖዶሱን መግለጫ በከፍተኛ ደረጃ መሞገታቸው ተዘግቧል፡፡ ከእኒህም አንዱ የኾኑት የቅ/ሲኖዶሱ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፣ የማክሰኞውን ስብሰባ ትተው መውጣቸው የተገለጸ ሲኾን፤ ዘግይቶ በደረሰን ዜና መሠረት ደግሞ ከዋና ጸሐፊነት ሓላፊነታቸው የመልቀቂያ ደብዳቤ ለዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪኩ ማቅረባቸው ተሰምቷል፡፡

ዋና ጸሐፊው በወቅታዊ አጀንዳ በተላለፈው ውሳኔ በአቋም ከመለየታቸው ባሻገር፤ ‹‹በጽ/ቤቱ ስም ሳላውቃቸው የሚወጡ ደብዳቤዎች አሉ›› የሚለው አቤቱታቸው በሓላፊነታቸው ላለመቀጠል እንደምክንያት እንደሚጠቅሱ የመንበረ ፓትርያሪኩ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ ብፁዕ ዋና ጸሐፊው ሳላውቃቸው በጽ/ቤቱ ስም ይወጣሉ ካሏቸው ደብዳቤዎች መካከል ዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪኩ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴርን እገዛ ጠይቀውበታል የተባለው ደብዳቤ እንደሚገኘበት ተመልክቷል፡፡

በዚህ ደብዳቤ ዐቃቤ መንበረ ፓትርያሪክ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል የጠቅላይ ቤተክህነቱ ከፍተኛ ሓላፊዎች ሥራቸውን እንዳይሠሩና ምርጫውን በአስቸኳይ እንዳያካሂዱ ዕንቅፋት እየፈጠሩባቸው በመኾኑ፣ መንግሥት እገዛ እንዲያደርግላቸው መጠየቃቸው ነው የተዘገበው፡፡ ዐቃቤ መንበሩ የመንግሥትን እገዛ በደብዳቤ መጠየቃቸውን ተከትሎ ቅድሚያ የዕርቀ ሰላሙ ጉዳይ እንዲቋጭና ወደ ምርጫው እንዲገባ በሚበዙት ተሳታፊዎች ተይዞ የነበረው አቋም እንዲዳከም አስተዋፅኦ ማድረጉን ነው ታዛቢዎች የሚናገሩት፡፡ ለጋዜጠኞች ጥያቄዎች ምላሽ ከሰጡት የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከፍተኛ ሓላፊዎች አንዱ ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ፣ ዐቃቤ መንበሩ ለመንግሥት የጻፉት ደብዳቤው እንዳለ አምነው ይዘቱ ግን ‹‹በአጠቃላይ ስለ አንዳንድ ሥራዎች ሂደት እንጂ ከዐቢይ ጉባኤው ጋር የሚገናኝ ጉዳይ የለውም›› ብለዋል፡፡

ከ1999 ዓ.ም ጀምሮ በሦስት ዙር ሲካሄድ ስለቆየው የሰላምና አንድነት ጉባኤ ቀጣይነት የተጠየቁት ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ፣ ‹‹ከግማሽ መንገድ በላይ ተኪዷል፤ እንደ አቋም የኢትዮጵያው ሲኖዶስ መኾን መደረግ ያለበትን የሰላም አቋም አሟጦ ጨርሷል፤ ከዚህ በላይ የሚደረግ ነገር የለም›› ቢሉም ቀደም ሲል ከነበረው አደራዳሪ አካል ይልቅ÷ ግራ ቀኙን አይቶ የተለያዩ አማራጭ ሐሳቦችን ደፍሮ ለማቅረብ፣ ተጽዕኖ ለማሳደር የሚችል ብቃትና አቅም ያለው አካል ሲገኝ ቅ/ሲኖዶሱ እያጠና የመጨረሻዋ ሰላም እስክትረጋገጥ ድረስ ይቀጥልበታል የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በቅ/ ሲኖዶሱ መግለጫ ላይም እንደተመለከተው÷ በውጭ ያሉት አባቶች የተሰጠውን የሰላም ዕድል ተጠቅመው ወደ ሰላሙና አንድነቱ ለመምጣት ፈቃደኞች ኾነው እስከተገኙ ድረስ ኹኔታዎች ሲመቻቹ ቀደም ሲል የተጀመረውን የሰላምና ዕርቅ ሂደት እስከ መጨረሻው ለመቀጠል አሁንም ዝግጁ መኾኑን አረጋግጧል፡፡

ቅ/ሲኖዶሱ በወቅታዊ የቤተ ክርስቲያኒቱ ጉዳይ ላይ ያደረገው ውይይትና ያሳለፈው ውሳኔ÷ ከኅዳር 26 - 30 ቀን 2005 ዓ.ም በዳላስ ቴክሳስ ለሦስተኛ ጊዜ በተካሄደው ጉባኤ አበው ላይ የተሳተፉት ልኡካን ባቀረቡት አጠቃላይ ሪፖርት ላይ የተመሠረተ መኾኑ በቅ/ሲኖዶሱ መግለጫው ላይ ተመልክቷል፡፡ በዳላሱ ድርድር ላይ ለዕርቁና ሰላም ስምምነቱ አለመፈጸም እንደዋነኛ ምክንያት የተጠቀሰው÷ ‹‹የቀድሞው ዐራተኛ ፓትርያሪክ መንበራቸው ክፍት ስለሆነ ወደ መንበራቸው መመለስ አለባቸው፤ በሙሉ የፓትርያሪክነት ሥልጣንም ቤተ ክርስቲያንን መምራት አለባቸው፤ ይህ የማይደረግ ከኾነ ግን አንስማማም›› የሚለው በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ አባቶች አቋም ነው፡፡

ቅ/ሲኖዶሱ ይህን አስመልክቶ በመግለጫው በሰጠው ማብራሪያ÷ ከዛሬ ኻያ ዓመታት በፊት የኢትዮጵያ ዐራተኛ ፓትርያሪክ የነበሩት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስ በወቅቱ ባደረባቸው ሕመም ነሐሴ 18 ቀን 1983 ዓ.ም በጠሩት አስቸኳይ የቅ/ሲኖዶስ ጉባኤ ሥልጣናቸውን ለማስረከብ መጠየቃቸውን አስታውሷል፡፡ ይኹንና ቅ/ ሲኖዶስ የቀድሞው ፓትርያሪክ በሕክምናም በጠበልም እየተረዱ ሊድኑ እንደሚችሉና ሐላፊነታቸውን ይዘው እንዲቀጥሉ ፈቃዳቸው እንዲኾን ቢለምናቸውም ሐሳባቸውን ከማጽናት በቀር ተለዋጭ መልስ እንዳልሰጡት ገልጧል፡፡

በመኾኑም ጉዳዩ በጥልቀት ሲጠና ሰንብቶ ነሐሴ 28 ቀን 1983 ዓ.ም የቀድሞውን ዐራተኛ ፓትርያሪክ ጥያቄ ተቀብሎ ሥልጣኑን መረከቡን፣ ኾኖም ግን ፓትርያሪኩ ሓላፊነታቸውን ለመወጣት የሚችሉበት ዕድል እንዳለ የሚጠቁም ፍንጭ ለማግኘት ለዐሥር ወራት ያህል ቢጠብቅም ባለመስጠታቸው ለኑሯቸው የሚያስፈልገውን ሁሉ፣ ደመወዝም መኪናም ፈቅዶላቸው በገዳም በጠበል እየታገዙ፣ በሕክምናም እየተረዱ በጸሎት ተወስነው እንዲኖሩ መወሰኑን አውስቷል፡፡ ከዚህ በኋላ ቤተ ክርስቲያን ያለመሪ ለብዙ ጊዜ እንድትቆይ ማድረግ የሚያስከትለውን ጉዳት በመገንዘብ የአምስተኛው ፓትርያሪክ ምርጫ እንዲካሄድ ግንቦት አራት ቀን 1984 ዓ.ም መወሰኑን ጠቅሷል፡፡

ይህ በዚህ እንዳለ አራት ሊቃነ ጳጳሳት ከሀገር ውስጥና ከውጭ አህጉረ ስብከት ከቤተ ክርስቲያናቸው ተነጥለው ሲወጡ፣ ዐራተኛ ፓትርያሪክ የነበሩትም በሞያሌ በኩል ኬንያ ገብተው ለሰባት ዓመት ከቆዩ በኋላ፣ ሁሉም በሰሜን አሜሪካ ተሰብስበው በታሪክ ታይቶም ተሰምቶም የማይታወቅ ድርጊት በመፈጸም በስደት አገር ሲኖዶስ አቋቁመናል ማለታቸው ተገልጿል፡፡ ፓትርያሪክም ኾነ ሊቀ ጳጳስ ከአገር ውጭ ሲኖዶስ ማቋቋም ይቅርና ያለቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ አንድ የፋሲካ በዓል ከሀገሩና ከሀ/ስብከቱ ውጭ ማክበር በቀኖና ቤተ ክርስቲያን የተከለከለ በመኾኑ ስሕተቱን በመነጋገር ለማረም በታኅሣሥ ወር 1999 ዓ.ም ልኡክ ቢላክም አናነጋግርም ከማለት አልፎ፣ በዚያው ዓመት ወርኃ ጥር የኤጲስ ቆጶሳት ሹመት በማከናወናቸው የቤተ ክርስቲያንን ቀኖና ለማስጠበቅ ሲባል ቅ/ሲኖዶስ ቃለ ውግዘት ማስተላለፉን፣ ስማቸውንና ሐዋርያዊ ሥልጣናቸውን ማንሣቱን ጠቅሷል፡፡

ከዚህ በኋላ ጉዳዩ በዕርቅና በሰላም ተቋጭቶ በውጭ ያሉት አባቶች ወደሀገራቸውና ወደ ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲገቡ ለማግባባት ጥያቄ ያቀረቡ ወገኖችን ሐሳብ ተቀብሎ በሐምሌ 2002 ዓ.ም በሰሜን አሜሪካ ቨርጂኒያ በሦስተኛ ወገኖች የሐሳብ ልውውጥ ቢያደርግም ‹‹ከመሠረተ ጉዳዩ ጋር ተያያዥነት የሌለውና ያልተጠበቀ ቅድመ ኹኔታ›› በመቀመጡ ሰላምና አንድነቱ ሳይሳካ ቀርቷል ብሏል፡፡

ከዚህ በኋላ ቅ/ሲኖዶሱ ለሰላሙ መፋጠን ያጸደቀውን ‹‹ወሳኝ የኾነ የመጨረሻ የሰላም አቋም›› ሲዘረዘር÷ ዐራተኛው ፓትርያሪክ ወደ አገራቸው ተመልሰው፣ ደረጃቸውና ክብራቸው ተጠብቆ፣ የሚያስፈልጋቸው ሁሉ ተሟልቶላቸው፣ በመረጡት ቦታ በጸሎት ተወስነው እንዲኖሩ፣ ነባሮቹንም ኾነ በእነርሱ አንብሮተ እድ የተሾሙ አዲሶቹ አባቶች አስመልክቶም ቀኖናውን በቀኖና አሻሽሎ፣ ሐዋርያዊ ሥልጣናቸውን ሰጥቶ፣ ስማቸውን መልሶ፣ በሀገረ ስብከት መድቦ ለማሠራት ፈቃደኛ መኾኑን በየካቲት ወር 2004 ዓ.ም በአሪዞና ፊኒክስ በተካሄደው ጉባኤ ይፋ ማድረጉን አስረድቷል፡ ፡ ይኹንና አሁንም ከቤተ ክርስቲያን ጋር ተያያዥነት የሌላቸው ጉዳዮች በማንሣታቸውና የቀረበውንም ጥሪ ባለመቀበላቸው የተጠበቀው ሰላምና አንድነት ሊገኝ እንዳልቻለ አብራርቷል፡፡

የዐራተኛውን ፓትርያሪክ ስደት ከተለመደው የአባቶች ስደት ልዩ የሚያደርገው የቀድሞው ዐራተኛው ፓትርያሪክ መንበራቸውን ራሳቸው በመልቀቃቸውና በማስረከባቸው፣ ያለምንም ምክንያት ሀገራቸውንና ቤተ ክርስቲያናቸውን ጥለው ከአገር በመውጣታቸው፣ በስደት አገር ሲኖዶስ በማቋቋማቸው መኾኑን ቅ/ሲኖዶሱ በመግለጫው አትቷል፡፡

ቅ/ሲኖዶሱ የቀድሞውን ዐራተኛ ፓትርያሪክ በፓትርያሪክነት የሥልጣን ደረጃ የማይቀበልባቸውን ምክንያቶች ሲዘረዝርም፡- ‹‹ይህን የመሰለ ታላቅ መንፈሳዊ ሥልጣን ሲፈልጉ ተረከቡኝ፣ ሲፈልጉ መልሱኝ እየተባለ የሚከራከሩበት ባለመኾኑና ይህን ጥያቄ ማስተናገድ በቤተ ክርስቲያን ሥርዐተ አልበኝነት እንዲሰፍን መፍቀድ በመኾኑ፣ ቅ/ሲኖዶሱ ለምኗቸው አይኾንም ብለው ጥለው የሄዱ በመኾኑ፣ ከዚህም የታሪክ መዛግብት እንደሚመሰክሩትና የቅ/ሲኖዶስ አባላትም እንደሚመሰክሩት የቀድሞውን ዐራተኛ ፓትርያሪክ ከመንበረ ፓትርያሪኩ አስወጪም ወጪም ኾነው ድርጊቱን ያፋጠኑ በወቅቱ ሰብሳቢ የነበሩና ኋላም ከእነርሱ ጋር የነበሩት አባት እንጂ ሌላ ባለመኾኑ፣ አምስተኛው ፓትርያሪክ በሕገ ቤተ ክርስቲያን ተሹመው የተሠራው የኻያ ዓመታት ሥራ ደምስሶና ሠርዞ ወደኋላ በመመለስ ዐራተኛ ፓትርያሪክ ብሎ መቀበል ፍጹም የማይቻል በመኾኑ ነው›› ብሏል፡፡ ስለዚህም በመግለጫው በቀዳሚ ተራ ቁጥር በተገለጸው አቋሙ÷ ቅ/ሲኖዶሱ የቀድሞውን ዐራተኛ ፓትርያሪክ በፓትርያሪክነት የሥልጣን ደረጃ እንደማይቀበል በማያሻማ ኹኔታ በድጋሚ መወሰኑን አስታውቋል፡፡

የአገር ቤቱን ቅ/ሲኖዶስ መጠናቀቅ ተከትሎ በሰሜን አሜሪካ በሚገኙት የቀድሞው ዐራተኛ ፓትርያሪክና ሌሎች ሊቃነ ጳጳሳት በስደት የተቋቋመው ሲኖዶስ ተሰብስቦ በመምከር ላይ መኾኑ ታውቋል፡፡ በተለይም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ መርቆሬዎስን ‹‹በፓትርያሪክነት ማዕረግ ላለመቀበል በማያሻማ ኹኔታ በድጋሚ ወስኛለኹ›› ባለው በኢትዮጵያው ቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች በእጅጉ ማዘኑንም ገልጧል፡፡ የስብሰባው ተሳታፊ በኾኑት አንድ ሊቀ ጳጳስም ‹‹በሰሜን አሜሪካ ነጻና ገለልተኛ የኾነ ሲኖዶስ ይቋቋማል›› መባሉም ተዘግቧል፡፡

የሀገር ቤቱን ቅ/ሲኖዶስ ውሳኔዎች የሚተቹ ወገኖች፣ የቀድሞው ዐራተኛ ፓትርያሪክ በሕመም ምክንያት ሥልጣናቸውን እንደሚለቁ ቢያሳውቁም በብዙ አባቶች ምክር ወደ መንበራቸው ለመመለስ ወስነው እንደነበር፣ ኾኖም በወቅቱ ሰብሳቢ የነበሩት አባት ፈጥነው በሚዲያ እንዲሰጥ ባደረጉት መግለጫ ነገሩ መሰናከሉን በመጥቀስ÷ ‹‹ቅ/ሲኖዶስ በወቅቱ ለምኗቸው አይኾንም ብለው ጥለውት ሄደዋል›› የሚለውን የመግለጫውን ክፍል ይቃወማሉ፡፡

መግለጫው ሁሉም የቅ/ሲኖዶስ አባላት የሰጡበት ትችት ተካቶና ይኹንታቸውን አግኝቶ ለመውጣቱ ጥርጣሬ ያላቸው አስተያየት ሰጭዎች÷ ከፓትርያሪክ ምርጫው በፊት የዕርቀ ሰላሙን ሂደት ለማሳካት ተስፋው ጨርሶ ያልጨለመ በመኾኑ ሁሉም ወገኖች በየፊናቸው በተለያዩ መድረኮች የሚያደርጉትን ጥረት አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል፡፡ በእነርሱ አስተያየት በሁለቱም ‹ሲኖዶሶች› ውሳኔና መግለጫ የተነሣ የሰላሙ ሂደት ላይ ተስፋ ከተቆረጠ ‹‹የቤተ ክርስቲያን አንድነት ዳግም በማይመለስበት ኹናቴ በከፋ የመከፋፈል አደጋ ውስጥ ይወድቃል፡፡››

ሚዩዚክ ሜይዴይ "ፍልስፍና 1" በተባለው የብሩክ አለምነህ መጽሐፍ አንድ ርዕስ ላይ ውይይት እንደሚያደርግ አስታወቀ፡፡ ነገ አምስት ኪሎ በሚገኘው ብሔራዊ ሙዚየም አዳራሽ በሚካሄደው ውይይት ላይ "ማህበራዊ ሱሰኝነት" የሚለው ርዕስ የተመረጠ ሲሆን የመነሻ ሐሳብ በማቅረብ ውይይቱን የሚመራው የሙዚቃ ሃያሲ ሰርፀ ፍሬስብሀት ነው፡፡

በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ተሳታፊ የሚሆነው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ካሉት ጠንካራ ጎኖች አንዱ ምርጥ አጥቂዎችን መያዙ ነው፡፣ ቁልፍ ሚና ይኖራቸዋል ከሚባሉት አጥቂዎች ደግሞ የቅዱስ ጊዮርጊሱ አዳነ ግርማ እና የደደቢቱ ጌታነህ ከበደ ይገኙበታል፡፡ እነዚህ ሁለቱ አጥቂዎች ብሄራዊ ቡድኑ ለአፍሪካ ዋንጫ ዝግጅት ሲያደርግ በተቀመጠበት የኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል በማረፊያ መኝታ ቤታቸው ጎረቤታሞች ነበሩ፡፡ ሁለቱ ተጨዋቾች ኢትዮጵያ ከ31 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከሱዳን ጋር እዚህ አዲስ አበባ ጋር ባደረገችው የመልስ ጨዋታ በፈጠሩት ጥምረት ታሪክ ሰርተዋል፡፡ ጥቅምት 4 ቀን 2005 ተደርጎ በነበረው በዚሁ ታሪካዊ ፍልሚያ ኢትዮጵያ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የበቃችብትን ጎል አዳና በጭንቅላቱ ከመረብ ያሳረፈው ከጌታነህ ከበደ የተሻገረለትን ክሮስ በአግባቡ በመጠቀም ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የግራ መስመር ተመላላሽ ተጨዋቾች የሆኑት የደደቢቱ ምን ያህል ተሾመ እና የስዊድኑ ሴሪናስካ ክለብ ተሰላፊ ዩሱፍ ሳላህ ደግሞ ሌሎቹ የብሄራዊ ቡድናችን ምርጦች ናቸው፡፡አሉላ ግርማንም ሁላችንም እናውቃለን፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ እና የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወሳኝ የቀኝ ተመላላሽ ተጨዋች ነው፡፡ ሰሞኑን ከእነዚህ አምስት የብሄራዊ ቡድን ቁልፍ ተጨዋቾች ጋር በኢንተርኮንትኔንታል ሆቴል ተገናኝቻለሁ፡፡ በርግጥ 23ቱም የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ባነጋግር ፍላጎቴ ነበር፡፡ እንደ ዋና አሰልጣኙ ሰውነት ቢሻው አነጋገር ሁሉም ቋሚ ተሰላፊዎች፤ ወሳኝ ሚና የሚኖራቸው ኮከቦቻችን ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በ29ኛው አፍሪካ ዋንጫ አለችበት፡፡ አዳነ፤ጌታነህ፤ ዩሱፍ፤ ምንያህልና አሉላ በዚህ ዙርያ እና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች አስተያት ሰጥተውኛል፡፡

ጭውውታችንን በትውልድ ስፍራ ብንጀምርስ---ጌታነህ
የተወለድኩት በዲላ ነው፡፡ ዲላ በቡና ምርቷ ትታወቃለች፡፡ አምስት ኳስ ተጨዋቾችን ለኢትዮጵያ እግር ኳስ አፍርታለች፡፡ እነ ከፍያለሁ፤ ብርሃኔ አንለይ፤ ዳንኤል ደርቤ የዲላ ልጆች ናቸው፡፡አዳነ
እኔ የተወለድኩት በሃዋሳ በምትገኘው ኮረም የተባለች ሰፈር ነው፡፡ ኮረም ብዙ ኳስ ተጨዋቾች እና ሾፌሮችን ያፈራች ሰፈር ናት፡፡ እዚያ ኮረም ሜዳ የሚባል ስፍራ አለ፡፡ ያ ሜዳ በርካታ ተጨዋቾችን ወደ ኢትዮጵያ እግር ኳስ ያመጣና ለብሄራዊ ቡድን ያበቃ ነው፡፡ እነ ሙሉጌታ ምህረት፤ ዮናታን ከበደና ሌሎችም ከዚያ ነው የወጡት፡፡ምንያህል
ተወልድጄ ያደግኩት እዚሁ አዲስ አበባ ነው፡፡ ሰፈሬም መገናኛ አካባቢ 24 ቀበሌ ነው፡፡አሉላ
ትውልዴ በ6 ኪሎ ጃንሜዳ ሰፈር ነው፡፡
ኳስ ተጨዋችነትን የጀመራችሁት በልጅነት ነው ወይስ አዋቂ ከሆናችሁ በኋላ?አዳነ
ከልጅነቴ ጀምሮ ከኳስ ጋር ነው ያደግሁት እናም ታዋቂ ኳስ ተጨዋች የመሆን ህልም ነበረኝ፡፡ ይህን ህልም ይዤ አድጌያለሁ፣ አሁን እውን ስለሆነ በጣም ደስ ይለኛል፡፡ጌታነህ
እግር ኳስ ተጨዋችነት ሙያዬ እንደሚሆን ባላስብም በሰፈር ውስጥ እየተጫወትኩ ሳድግ ፍላጎቱ የተፈጠረ ይመስለኛል፡፡ ካደግኩ በኋላ ግን ሙያዬ እንደሚሆን እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ምንያህል
ታዳጊ ሳለሁ የፕሮጀክት ተጨዋች ነበርኩ። አንዳንዴ የብሔራዊ ቡድን ማሊያ ለልምምድ እንድለብስ ሰዎች ሲሰጡኝ አልፈልግም እላቸው ነበር፡፡ ወደፊት የራሴን መልበሴ አይቀርም ብዬ አስብ ነበር፡፡ በውስጤ ይህ እምነት ነበረኝ፡፡ አሁን እዚህ ደረጃ ደርሼ የሚያኮራ ሙያ ሆኖልኛል፡፡ አሉላ
ያደጉት በጃን ሜዳ አካባቢ ስለነበር ለስፖርቱ ቅርበት ነበረኝ፡፡ አባቴ በቀለም ትምህርት እንድገፋ ቢመክረኝም እግር ኳስን አዘውትሮ መጫወት አበዛ ነበር፡፡ በትምህርት ቤት የደረጃ ተማሪ ነበርኩ፣ በእግር ኳሱ በጣም እየገፋሁበት ስሄድ ግን ሙያዬ እንደሚሆን እያወቅሁ መጣሁ፡፡ዩሱፍ
ከልጅነቴ ጀምሮ ኳስ ተጨዋች መሆን እፈልግ ነበር፡፡ በቲቪ እያየሁ ያደግሁት ስፖርት ነው፡፡ ቤተሰቤ በተለይ አባቴ እንድማር ይፈልግ ነበር፡፡ ኳስ እንድጫወት የሚፈቀድልኝ በትምህርቴ ስበረታ ብቻ ነበር፡፡ በኋላ ግን በስዊድን ፕሮፌሽናል ሊግ ውስጥ ገብቼ አሁን ላለሁበት ደረጃ በቅቻለሁ፡፡ እናም የምከበርበት ሙያ ሆኖልኛል። ማንም እግር ኳስ ተጨዋች ትልቁ ዓላማው በብሔራዊ ቡድን ውስጥ መጫወት ነው፡፡ እኔም በስዊድን ወጣት ብሔራዊ ቡድን ውስጥ ተጫውቻለሁ፡፡
ወደ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ስገባ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ አሁን ደግሞ የመጀመርያው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ ልሳተፍ ነው፡፡ ወደ ኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የገባሁበትን የመጀመሪያ አጋጣሚ የፈጠረው አሰልጣኝ ስዩም ከበደ ነው፡፡ በኢሜልና በስልክ ባደረግነው ግንኙነት በምጫወትበት ክለብ ውስጥ ያለኝን ብቃት የሚያሳዩ የቪዲዮ ምስሎች እንድልክለት ስዩም ጠየቀኝ፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ፊልሞችን መመልከት እንደሚፈልግ ነገረኝ፡፡ በምጫወትበት የስዊድን ክለብ ሴሪናስካ ዘንድሮ እና ባለፈው የውድድር ዘመን ያደረግኋቸውን ጨዋታዎች የሚያሳዩ ፊልሞች ላኩኝ፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ፊልሞቹን ተመልክተው ወደ ኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በመቀላቀል ልሠራ እንደምችል በስልክ ነገሩኝ፡፡ በዚህ መንገድ ብሔራዊ ቡድኑን ለመቀላቀል ችያለሁ፡፡
ብሄራዊ ቡድኑ ለአፍሪካ ዋንጫ ካለፈ በኋላ ያገኛችሁት አጠቃላይ የገንዘብ ሽልማት ስንት ደረሰ?አዳነ
355ሺ ብር
ጌታነህ
335ሺ
ምንያህል
300ሺ ብር
አሉላ
350ሺ ብር
ከትልቅ ጨዋታ በፊት በየትኛውም ቡድን ውስጥ ተጨዋቾች መጨነቅና መወጠራቸው አይቀርም፡፡ ከሱዳን ጋር ወደ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ በተደረገው የመጨረሻው ፍልሚያ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች መብላትና መተኛት ሁሉ ተቸግረው ነበር ይባላል፡፡ አሁን ደግሞ ከ31 ዓመታት በኋላ ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ዋንጫ አልፋለች፡፡ የሚያጨናንቅ ነገር አለ?አዳነ
በሱዳኑ ጨዋታ እንቅልፍ ማጣታችንንና መጨነቃችንን የተናገርነው ከ31 ዓመታት በኋላ ኢትዮጵያ ወደ አፍሪካ ዋንጫ የምታልፍበት ወሳኝና የመጨረሻ ምእራፍ ላይ ደርሰን ስለነበር ነው፡፡ ታሪክ መስራት፤ ህዝባችንን ማስደሰት፤የሚሉትን ማሰብ ያስጨንቃል። አሁን ግን በከፍተኛ የራስ መተማመን ውስጥ ነው ያለነው። አንዴ ማለፋችንን ስላረጋገጥን ምንም አይነት ጭንቀት እና ጫና የለብንም፡፡ እንደውም ጫናው ለእነ ዛምቢያ ነው የሚሆነው፡፡ እኔ በበኩሌ አልጨናነቅም፡፡ ዛምቢያ አሁን ሻምፒዮናነቷን ለማስጠበቅ ትጨናነቃለች። እኛ ግን ማንም አያውቀንም፡፡ አለመታወቃችን ጭንቀት የሚፈጥረው በምድቡ ተቀናቃኞች ላይ ነው፡፡ጌታነህ
ከ31 ዓመታት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያን የምናሳልፍበት እድል በፈጠረው ፍልሚያ የነበረው ጭንቀት የተፈጠረው ቅድም አዳነ በዘረዘራቸው ምክንያቶች ነው፡፡ የተለየ የምጨምረው ቢኖር በወቅቱ ባይሳካልንስ ብለን መስጋታችንን ነው፡፡ ከጨዋታ በፊት በየሚዲያው "የመጨረሻው እድላቸው" ተብሎ መነገሩም ያስጨንቅ ነበር፡፡ አሁን ግን በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ መሳተፋችን በመረጋገጡ በምድብ የምናደርገው ውድድር ስለሆነ ብዙም የሚያስጨንቅ ነገር አለ ብዬ አላስብም፡፡ምንያህል
አሁን እየገባን ያለው ወደ አህጉራዊ ውድድር ነው። ባለፈው በሱዳን ጨዋታ ጭንቀት የተፈጠረብን ወደዚህ የውድድር ምዕራፍ ለመሸጋገር ወሳኝ ፍልሚያ ላይ በመድረሳችን ነበር፡፡ ወደ ታላቅ ምዕራፍ ለመሸጋገር ዋዜማ ላይ ስለነበርን ነው ከፍተኛ ጫና የተፈጠረብን፡፡ አሁን ስለአፍሪካ ዋንጫ ለማውራት የበቃነው ያንን ወሳኝ ፍልሚያ አልፈን ነው፡፡
በምድብ 3 የመክፈቻ ጨዋታ ስለምትገጥሟት ሻምፒዮኗ ዛምቢያ ወቅታዊ የአቋም ሁኔታ ምን መረጃ አላችሁ?አዳነ
ከፍተኛ ትኩረት የሰጠነው ካለፈው የአፍሪካ ሻምፒዮን ዛምቢያ ጋር የምናደርገው የምድቡ መክፈቻ ጨዋታን ነው፡፡ ሁላችንም እንደተከታተልነው ዛምቢያ በወዳጅነት ጨዋታዎች ተከታታይ ሽንፈት ስላጋጠማት በጥሩ አቋም ትገኛለች ለማለት ያጠራጥራል፡፡ በአንፃሩ የኛ ዝግጅት የተሳካ ነው፡፡ ሁለት የወዳጅነት ጨዋታዎች አሸንፈናል፡፡ በአንዱ አቻ ወጥተናል፡፡ በተለይ ከአፍሪካ ኃያል ቡድኖች አንዷ ከምትባለው ቱኒዚያ ጋር አቻ የወጣንበት ሁኔታ ጥንካሬያችንን ያጎላዋል፡፡ ከዚህ አንፃር የምድብ 3 የመክፈቻ ጨዋታ ከእኛ ይልቅ ፈታኝ የሚሆነው ለዛምቢያ ይመስለኛል፡፡ እነሱ ተሸብረው ይገባሉ። እኛ ግን ከዚህ በፊት ከሚያውቁን የተሻለ ጥንካሬ ይዘን እንገጥማቸዋለን፡፡
አዳነ እና ጌታነህ ሁለታችሁም የዋልያዎቹ ወሳኝ አጥቂዎች እንደመሆናችሁ አንድ የታዘብኩትን ሁኔታ እንዴት እንደምታዩት ማወቅ እፈልጋለሁ፡፡ ከ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ አራት ምድቦች መካከል ምድብ 3 በጥንካሬው ብቻ ሳይሆን በርካታ ምርጥ አጥቂዎች የተሰባሰቡበት ሆኖ ይለያል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የአጥቂ መስመር ከመቸውም ጊዜ በላቀ ሁኔታ በምርጥ ስብስብ የተዋቀረ ይመስለኛል፡፡ የናይጄርያ ብሄራዊ ቡድንም የአፍሪካ ዋንጫውን ምርጥ አጥቂዎች በመያዝ የሚጠቀስ ነው፡፡ በዛምቢያም ቢሆን አንዱ ልዩ ጥንካሬ የአጥቂ መስመሩ ነው፡፡ በፈረንሳይ ሊግ ምርጥ የተባሉ አጥቂዎችን የያዘውና ከፍተኛ ልምድ ያላቸው የፊት መስመር ተሰላፊዎችን ያካተተው የቡርኪናፋሶ ቡድንም የሚናቅ አይሆንም። ይህን የምድብ 3 የአጥቂዎች መብዛት እንዴት ታነፃፅሩታላችሁ?ጌታነህ
ብዙ የማውቃቸው የናይጄርያ አጥቂዎችን ቢሆንም አንዳንድ የዛምቢያ አጥቂዎችንም አውቃለሁ፡፡ ይሁንና የእኛ ቡድንም በአጥቂዎቹ ብዙ የሚተናነስ አይደለም። የቡድናችን ሁላችንም አጥቂዎች ጠንካሮች ነን፡፡ በየጨዋታው ሁሉም አጥቂዎች ጎል እያገባን ቆይተናል። አንዳችን ገብተን ጎል ማስቆጠር ቢያዳግተን ተቀይረን በመግባት ጎል እያገባን እየወጣን ነው፡፡ አጥቂ ሆነህ ሜዳ ስትገባ ጎል ማግባት አለብህ። በእኛ ቡድን ያሉ አጥቂዎች ጥንካሬም ይህንኑ ሃላፊነት በአግባቡ እየተወጣ ነው። ሁላችንም ወደ ሜዳ የምንግባው በአንድ ሆነ በሌላ አጋጣሚ ጎል ለማስቆጠር እምነትና ጥንካሬ ይዘን ነው፡፡
አዳነ
ከዚህ በፈት የነበሩ የብሄራዊ ቡድን አጥቂዎች ጎል የማግባት ችግር ነበረባቸው፡፡ አሁን ያለን አጥቂዎች ግን ለውጤት የሚያበቁ ወሳኝ ጎሎችን በሜዳችን ሆነ ከሜዳ ውጭ ለማስቆጠር ብዙ ችግር የለብንም፡፡ የሁላችንም ወቅታዊ ብቃት ይህን ለማለት የሚያስተማምን ይመስለኛል፡፡ ቡድናችን ድሮ ከሜዳ ውጭ አያገባም ነበር፡፡ ያ ነገር አሁን ባለው የአጥቂ ትውልድ ተሰብሯል፡፡ ለዚህም ነው በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ጎል ለማግባት ብቃቱ እንዳለን በእርግጠኝነት ነው የምናገረው። በወዳጅነት ጨዋታዎቹ እንደታየውም በርካታ የግብ ሙከራዎችንም እናደርጋለን፡፡ በቡድናችን ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ የማድረግ ብቃት እና ጥንካሬ ያላቸው አጥቂዎች መኖራቸውን ማንም አይክደውም፡፡ ስለሆነም በተቃራኒ ቡድኖች ስላለው የአጥቂ መስመር ጥንካሬ ብዙ ማሰብ አልፈልግም፡፡ የኢትዮጵያ አጥቂዎች ጥንካሬ በአፍሪካ ዋንጫው ማጣርያ ብቻ ሳይሆን በዓለም ዋንጫው ማጣርያ ሲታይ የቆየ በመሆኑ ይህ ጥንካሬ አሁንም በአፍሪካ ዋንጫው ቀጥሎ ለውጤት እንደሚያበቃን ነው ተስፋ የማደርገው፡፡
እንግዲህ የአፍሪካ ዋንጫን ለየት ከሚያደርጉት ባህርያት መካከል ጎል ከገባ በኋላ በየቡድኖቹ ተጨዋቾች የሚታየው የደስታ አገላለፅ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ጐል ሲያገባ ደስታውን እንዴት ለመግለፅ ታስቧል?አዳነ
እንደ ብዙ የአፍሪካ አገራት ኢትዮጵያም ብዙ ባህል ያላት አገር ናት እና መልካም ገፅታዋንና እና ባህሏን የሚያስተዋውቅ የደስታ አገላለፅ ለማድረግ እንሞክራለን። በዚህ ታላቅ መድረክ ጎል በማግባት የሚፈጠረውን አጋጣሚ ማንነታችንና አገራችንን ለማስተዋወቅ ብንችል ደስ ይለናል፡፡ ሁሉም ይህን ያስባል ብዬ እገምታለሁ፡፡ በቡድን ደረጃ እንዲህ አይነት የጎል ደስታ አገላለፅ እንስራ ብለን የመከርነው ነገር የለም፡፡ ግን ቀላል ነገር ነው። በየጨዋታው መግቢያ ላይ ተመካክረን የምናደርገው ነው፡፡ጌታነህ
ልክ ነው ከወዲሁ የተዘጋጅንበት ነገር የለም፡፡ እኔ ግን የማስበው ጎል ያገባው ተጨዋች የሚያሳየውን ደስታ አገላለፅ በመከተል የምንፈልገውን ጭፈራ የምናሳይ ይመስለኛል፡፡ አሁን አዳነ አግብቶ ኦሮምኛ ቢጨፍር እሱን አጅበን ነው ኦሮምኛ የምንጨፍረው። ጎል አግቢው ያሳየውን የደስታ አገላለፅ ሁላችንም የቡድኑ አባላት በደስታ የምንጋራው ይመስለኛል፡፡ አስቀድመን ብንዘጋጅም ባንዘጋጅም በአንድ መንፈስ ማራኪ ደስታ አገላለፅ እንደምናሳይ አውቃለሁ፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በተለይ ባለፉት ሁለት ዓመታት ስኬታማ እየሆነ መጥቷል፡፡ የዚህ ልዩ ብቃት ምስጢር ምንድነው? የቀድሞዎቹ ቡድኖች ግብ አያስቆጥሩም ነበር፤ ከሜዳ ውጭ ማሸነፍም ሆነ ነጥብ መጋራት በጣም ሲከብዳቸው ቆይቷል። አሁን ግን ከሜዳ ውጭ ግብ ማስቆጠርና ነጥብ ይዞ መውጣት እየተለመደ ነው፡፡ አስቀድሞ ቢገባም ከኋላ ተነስቶ ግብ በማስቆጠር ውጤት ማስጠበቅ እየተቻለ ነው። ይህ አይነቱ ስኬት በአጋጣሚ የሚገኝ አይደለም፡፡ ለሚታዩት ለውጦች አበይት ምክንያቶች ምንድን ናቸው?አዳነ
የመጀምሪያው ምክንያት ይህን ቡድን ለረጅም ጊዜ ሲያሰለጥን የቆየው አንድ አሰልጣኝ መሆኑ ነው። ከዚህ በፊት እንደሚታወቀው የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ በየጊዜው ይቀያየራል፡፡ ይህም ቋሚ ቡድን ለመስራት የሚያመች አልነበረም፡፡ የአሰልጣኞች መቀያየር በየጊዜው በአዳዲስ ልጆች ወጥ አቋም ሊኖረው የማይችል ቡድን መስራትን ያስገድዳል፡፡ ይህ ደግሞ የውጤት እንቅፋት ነው፡፡ አሁን ያለው ብሄራዊ ቡድን ለሁለት ዓመታት በአንድ አሰልጣኝ ሲገነባ እና ሲሰለጥን የቆየ ነው። ብዙዎቻችን አንድ ላይ ሆነን እሰከ 10 ጨዋታዎች አድርገናል። ይሄ ሁኔታ የቡድኑ ተጨዋቾች አብረን በመስራት ለረጅም ጊዜ እንድንቆይ ከማድረጉም በላይ፣ ከፍተኛ መግባባት እና መተዋወቅ ፈጥሮልናል፡፡ ጥሩ እና አሳማኝ ብቃት ያላቸው አዳዲስ ተጨዋቾች በየጊዜው ወደ ብሄራዊ ቡድኑ ይገባሉ፡፡ በየጨዋታው አዲስ ቡድን አዲስ ስብስብ እየተሰራ አልነበረም፡፡ ለየትኛው ቡድን ውጤታማነት ይሄ አይነቱ የቡድን መዋቅር እጅግ ወሳኝ ሚና ይኖረዋል፡፡ጌታነህ
በአዳነ አስተያየት ላይ የምጨምረው ቢኖር ባለፈው አንድ አመት ተጨዋቾችን በየጊዜው መቀያየር እና ቡድን ማፍረስ አልነበረም፡፡ ይህ ቡድን አዲስ ተጨዋች ቢጨመርበት እንጅ ባለፉት 10 ጨዋታዎች ቋሚ ልጆች አብረን ቆይተናል፡፡ ከዚህ ቀደም በየጊዜው አሰልጣኝ ሲቀያየር፤ ወደ ብሄራዊ ቡድን የሚመጣው አዳዲስ ስብስብ ችግር ነበረው፡፡አዳነ
የአመጋገብና የስነልቦና ባለሙያዎች ከቡድኑ ጋር መስራታቸውም ሌላ ለውጥ ነው፡፡ እነዚህ ሁሉ ሁኔታዎች በቡድኑ የተሰባሰቡ ተጨዋቾች በሁሉም ረገድ ተዋህደው እና ተግባብተው በአላማ እንዲሰሩ ምክንያት ነበር። የትኛውም የቡድን ተጨዋች ከሌላ የቡድን አጋሩ ጋር የመግባባት ችግር የለበትም፡፡ በሜዳ ላይም ሆነ ከሜዳ ውጭ ባለ ብቃት እና ባህርይ የሚጣጣም እና የሚግባባ ነው፡፡ አሁን በብሄራዊ ቡድን ያለው የተጨዋቾች ስብስብ ተበትኖ አንድ ሳምንት ልምምድ ሳይሰራ ቆይቶ በድጋሚ ቢሰባሰብ በቀላሉ ተቀናጅቶ ለመስራት አይከብደውም፡፡የብሄራዊ  አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች ብሄራዊ ቡድኑ ለአፍሪካ ዋንጫ ያለፈው በተደረገው የማጣርያ ድልድል በተፈጠረለት ምቹ እድል ነው ይላሉ፡፡ የተወሰኑ ደግሞ ስኬቱን ተዓምር ያደርጉታል፡፡ ለዚህ አፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ወሳኝ አጋጣሚ የምትሉት ምንድነው? አዳነ
በአፍሪካ ዋንጫው ማጣርያ በተለይ ከሜዳ ውጭ ከቤኒን ጋር ተጋጥመን በአቻ ውጤት ነጥብ ተጋርተን ስንወጣ ወሳኙ አጋጣሚ ተፈጥሯል ብዬ አምናለሁ። ከቤኒን ጋር እዚህ በሜዳችን 0ለ0 ወጥተን፣ በመልስ ጨዋታ ወደዚያ አቅንተን ከሜዳችን ውጭ፤ በሌሎች ደጋፊዎች ጩኸት ተከበን የተጫወትን ሲሆን፣ አንድ እኩል በመውጣት ወደ ቀጣይ የማጣርያ ምእራፍ ያለፍነው ከፍተኛ መስዕዋትነት ከፍለን ነው፡፡ጌታነህ
በማጣርያው ያደረግናቸው ጨዋታዎች በሁለት ምእራፍ የተደረጉ ቢሆንም አራት ጨዋታዎች አድርገናል። ይህ ማለት እንግዲህ ማጣርያው በምድብ የተዘጋጀ ቢሆን የቀረን ተጋጣሚ አንድ አገር ብቻ ብቻ መሆኑ ነው፡፡ በምድብ ማጣርያ ሦስት፤ በሜዳችን ሶስት ከሜዳ ውጭ ሦስት በአጠቃላይ ስድስት ጨዋታዎች ነበር የሚደረገው። በሁለት ዙር በተካፈልነው ማጣርያ ያደረግነው ሁለት በሜዳችን ሁለት ደግሞ ከሜዳ ውጭ አራት ጨዋታዎች ነው፡፡ ስለዚህ የማጣርያው አይነት ብዙም እድል የሚፈጥር አለመሆኑን መረዳት ያስፈልጋል።አሉላ
ለአፍሪካ ዋንጫ ያለፈው ብሔራዊ ቡድን እንደ ቤተሰብ የተጠናከረ የቡድን ስብስብ አለው። ውጤታችን የህብረት ነው፡፡ በአገር ፍቅር መንፈስ የተገኘ ነው። በስነልቦናና በስነምግብ የነበረን አጠቃላይ ዝግጅትና አደረጃጀት ከፍተኛ ኃላፊነት ውስጥ ከቶን ነበር። ብሔራዊ ቡድኑ በከፍተኛ ልምምድ ነው ተገቢውን ብቃትና ጥንካሬ ሊያገኝ የቻለው፡፡
የአትዮጵያ እግር ኳስ ለበርካታ አመታት በፌደሬሽን ውዝግብ በአገር ውስጥ ሊግ አለመጠናከር እና በተለያዩ ምክንያቶች ተዳክሞ ቆይቷል፡፡ በእግር ኳሱ ዛሬ ለተከፈተው አዲስ የለውጥ እና የእድገት ምእራፍ በር ከፋች የሆኑ ክስተቶች እና ምክንያቶችን ልትነግሩኝ ትችላላችሁ?አዳነ
ካለፉት አምስት አመታት ወዲህ ለውጦች እየተፈጠሩ መጥተዋል፡፡ በተለይ አስቀድሞ የነበረው የፊርማ ክፍያ 35 ሺ ነበር፡፡ በ2000 ዓም እኔ ወደ ጊዮርጊስ ስገባ ወደ 70ሺ ብር አደገ፡፡ ይህ ብሩህ ተስፋ ነበር፡፡ ለብዙ ተጨዋቾች መነሳሳትም ምክንያት ሆኗል፡፡ አሁን የፊርማ ክፍያ በአማካይ እስከ 400ሺ ብር ነው፡፡ ከፍተኛው እስከ 800ሺ ብር ደርሷል። ተጨዋቾች ጠንክሮ ለመስራት ይሄ ጥቅም በቂ ምክንያት ይሆናቸዋል፡፡ጌታነህ
ከጊዮርጊስ ክለብ ባሻገር የፊርማ ክፍያ በሌሎች ክለቦች ባለሃብቶች ትኩረት ተሰጥቶት ይሰራበት መጀመሩም ሌላው የለውጥ በር ከፋች ይመስለኛል። አሁን እኔ በደደቢት ክለብ በ75ሺ ብር ፊርማ ስገባ የባለሃብቶች ትኩረት ወደሌሎች ክለቦች መስፋፋቱን ያሳየ ነበር፡፡ በደደቢት ክለብ ለተጨዋቾች ብቃት ማደግ ይሄው የፊርማ ክፍያ ከፍተኛ መነሳሳት እየፈጠረ ነው። ሁላችንም ተጨዋቾች ጠንክረን የምንሰራው ነገ ደህና የፊርማ ብር በማግኘት ለመጠቀም ነው፡፡ በብዙ ክለቦች የተጨዋቾች ደሞዝ እኩል ነው፡፡ የሚለያየን የፊርማው ክፍያ ነው፡፡አሉላ
እግር ኳስ ከኢኮኖሚ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ በአገራችን እግር ኳስ የመዕለ ንዋይ ፍሰት እየጨመረ መምጣቱ እየታየ ላለው ለውጥና እድገት ጉልህ አስተዋጽኦ አበርክቷል፡፡ የአውሮፓ እግር ኳስ ከፍተኛ ደረጃ የደረሰው በገንዘብ አቅም ነው፡፡ የዚህ ዘመን ተጨዋቾች በእግር ኳስ ከፍተኛ ስኬት እያገኛችሁ ነው፡፡ ስኬታማነት አድናቆት እና ዝና ያመጣል፡፡ ዝነኛ መሆን ደግሞ አንዳንዴ ያዘናጋል፡፡ አዳነ
ስኬታማ ሲሆኑ አድናቆት እንደሚኖር ሁሉ፤ ስኬታማ ባለመሆንም ትችት ያጋጥማል። ስለሆነም አድናቆት ለእኔ ብዙ አይገርመኝም፡፡ አድናቆቱንም ትችቱንም ተላምጄዋለሁ፡፡ አድናቆት የሚያዘናጋ አይመስለኝም፡፡ ያው እንደምታውቀው የምጫወትበት ቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ብዙ ደጋፊ ያለው ነው፡፡ አንዳንዴ በጨዋታ ላይ ሃትሪክ ስሠራ ከፍተኛ አድናቆት አገኛለሁ። ደጋፊዎች ያለናንተ ሰው የለም ሁሉ ይሉናል፡፡ በጨዋታ ላይ ደጋፊዎች ስሜን እየጠሩ ሲያወድሱኝ በውስጤ ጥሩ ስሜት ይፈጥራል። ግን አልኮፈስበትም፡፡ የደጋፊ ባህርይ ነገ ጥሩ ካልሆንክ ደግሞ ወደ ስድብ ይቀየራል፡፡ በርግጥ ለምን ተሰደብኩ ብዬ አልናደድም፡፡ ደጋፊዎች በብቃቴ ጥሩ አለመሆን ተበሳጭተው የፈለገውን ቢሰድቡኝ ምንም አይመስለኝም፡፡ ቤተሰቤን ሲነኩ ግን ደስ አይለኝም፡፡
እግር ኳስ ስሜታዊ ያደርጋል፡፡ በስሜት የምትሳደበውና የምትተቸው ደግሞ ጥላቻ ነው ብዬ አላስብም፡፡ አሉላ
አሁን የደረስንበት ደረጃ ላይ ለመድረስ ብዙ መስዋዕትነት ከፍለናል፡፡ ያገኘነው ስኬት ደግሞ ብዙ አድናቆት አትርፎልናል፡፡ ምንያህል
ከታዳጊነቴ ጀምሮ በርካታ ድጋፍ ባለው የቡና ክለብ መጫወቴ ከአድናቆት ጋር አላምዶኛል፡፡ አድናቆት ኃላፊነትን ይጨምራል፡፡ በምትሠራው፣ በምታደርገው ሁሉ ጥንቁቅ ያደርግሃል፡፡ አድናቆት ክብር ያመጣል፡፡ እናም በክብር እንቀበለዋለን፡፡ ዩሱፍ
የኢትዮጵያ ህዝብ ድጋፍ በጣም ደስ የሚል ነው። በደቡብ አፍሪካም ብዙ ድጋፍ እንደሚጠብቀን አውቃለሁ፡፡ አድናቆት ለተሻለ ውጤት ያነሳሳል፤ ትበረታታለህ፡፡ በጣም ደስ ይልሃል፡፡ የተሻለ ትሠራለህ። በሙያህ አድናቆት እንዲኖርህ ትፈልጋለህ፡፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድኑን በተሳካ ሁኔታ ለመቀላቀል በመቻሌ የክለቤ ኃላፊዎች፣ የቡድን አጋሮቼ እና በስዊድን ያሉ ቤተሰቦቼ እጅግ በጣም ተደስተዋል፡፡ እርግጠኛ ነኝ፣ ብዙዎቹ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ተሰልፌ በደቡብ አፍሪካ በሚደረገው 29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ስሳተፍ በትኩረት ሁሉንም ይከታተላሉ፡፡
እንግዲህ የኢትዮጵያ ህዝብ ስፖርት አፍቃሪ ነው። ባለፉት 30 ዓመታት አትሌቶች በኦሎምፒክና በዓለም ሻምፒዮና መድረክ ባስመዘገቡት ውጤቶች ሲኮራና ሲደሰት ኖሯል፡፡ አሁን የእናንተ ትውልድ ለአፍሪካ ዋንጫ ካለፈ በኋላ በእግር ኳሱ እያበደ ነው፡፡ በኢትዮጵያ ተወዳጅ ስፖርት እግር ኳስ ነው አትሌቲክስ?ጌታነህ
ለኢትዮጵያ ህዝብ ተወዳጁ ስፖርት እግር ኳስ ነው የሚመስለኝ፡፡ ለአፍሪካ ዋንጫ ባለፍን ወቅት በመላው አገሪቱ ህዝቡ አደባባይ ወጥቶ ደስታውን የገለፀበትን ሁኔታ ስትመለከት ይህን ለማለት ያስደፍርሃል፡፡ አዳነ
እግር ኳስ የስፖርቶች ንጉስ ነው፡፡ ለምን ብትለኝ እግር ኳስ የቡድን ስራን መሠረት አድርጐ ውጤት የሚገኝበት መሆኑ ተወዳጅ ያደርገዋል፡፡ ሩጫ ብዙውን ጊዜ የአንድ ሰው ጥረት የሚታይበት ነው፡፡ እግር ኳስ የ90 ደቂቃ ልፋት፣ የህብረት ትግል የሚታይበት ነው፡፡ የፉክክር ደረጃውም ከፍተኛ መዝናናት የሚፈጥር ስለሆነ እግር ኳስ ከሩጫ ይልቅ ተወዳጅ ይመስለናል፡፡ ዮሴፍ
በልቤ እግር ኳስ የማስበልጥ ቢሆንም ለኢትዮጵያውያን አትሌቲክስ ኩራት መሆኑን አውቃለሁ፡፡ እግር ኳስ ግን እጅግ ግዙፍና ትልቅ ስፖርት ነው፡፡ ምን ያህል
የህዝቡን ቀልብ የሚስበው እግር ኳስ ነው፡፡ በፊት በውጤቱ አለመኖር ፍቅሩ ቀንሶ ሊሆን ይችላል። አሁን የተገኘው ስኬት የኢትዮጵያ ህዝብ ለእግር ኳስ ፍቅር የተገዛ መሆኑን አስመስክሯል፡፡ እግር ኳስ ቅጽበታዊ ውሳኔን የሚጠይቅ፣ ከፍተኛ የፉክክር ደረጃ ያለው መሆኑ ልዩ ስፖርት ያደርገዋል፡፡
እስቲ በቅጽል ስያሜዎች ዙሪ እናውራ፡፡ የብሔራዊ ቡድን ተጨዋቾች ልዩ ልዩ ቅጽል ስሞች አላቸው፡፡ አሁን አዳነ አዴ፣ ወፍጮ ይሉሃል፣ ጌታነህስ ማን ብለው ነው የሚጠሩህ? አዳነ
ወፍጮ ብለው የሚጠሩኝ ደጋፊዎች ምን ማለታቸው እንደሆነ ከሌላ ነገር ጋር የሚያያዙት አሉ፡፡ እኔ ግን እንደስድብ የሚቆጠር ቅጽል ስያሜ ቢሆን እንኳን ምንም አይመስለኝም፡፡ አሁን የቡና ደጋፊዎች ወፍጮ ብለው እየጠሩ ሊሰድቡኝ ሲሞክሩ የሚገርምህ እልህ ውስጥ ገብቼ ከፍተኛ ውጤት ለማግኘት እነሳሳለሁ፡፡ ጌታነህ
አሁን አዳነን ወፍጮ ሲሉት ብዙ ምግብ ይበላል ከማለት ጋር የሚያያዙት ይኖራሉ፡፡ ይህ ስም የወጣለት ግን በሜዳ ላይ ሲጫወት በነበረው ሚና ነው፡፡ በአንድ ጨዋታ ላይ አዳነ ተሰልፎ የተቃራኒ ቡድን ተጨዋቾችን እየተጋፈጠና እየተጋጨ ሲጫወት ተመልክተው ነው አሰልጣ ሰውነት ይሄን ስም ያወጡለት፡፡ ስላደነቁት የወጣ ቅጽል ስም መሆኑ መታወቅ ይኖርበታል፡፡ ለነገሩ አዳነ ለብዙ የቡድን ተጨዋቾች ቅጽል ስም በማውጣትም ይታወቃል፡፡ እኔን አሁን ገዬ ነው የሚለኝ፡፡ አዳነ
በቅጽል ስም ሰው የምጠራው ሙሉ ስም መያዝ ልማዴ አልሆን ብሎ ነው፡፡ በተለይ በጨዋታ ላይ ከቡድን አጋሮቼ ጋር ለመግባባት እዚያው የመጣልኝን አጠራር እጠቀማለሁ፡፡ የቡድን ልጆች ይህን አጠራሬን ሰምተው ያፀድቁታል፡፡ አሁን ጌታነህን ኳስ እንዲያቀብለኝ ስፈልግ ጌታነህ ብዬ ከምጠራው የመጀመሪያውን ፊደል "ገ" እና ለማቆላመጥ "ዬን" ጨምሬ ገዬ ብዬ እጠራዋለሁ፡፡ ለአንዳንዶቹ ደግሞ ከአጨዋወታቸው እና ከድርጊታቸው ተነስቼ ስም አወጣላቸዋለሁ፡፡ አሁን አምበላችንን ደጉን "ስለ"ብዬ የምጠራው፡፡ ዩሱፍ
ብሄራዊ ቡድኑን ከተቀላቀልኩ በኋላ ሜዳ ላይ ብቻዬን ኳስ ሳንጠባጥብ አሰልጣኙ ተመልክተው በቃ የውጭ አገር ሰው መሆንህ ቀርቷል፡፡ አሁን አበሻ፣ እንደውም ጐንደሬ ሆነሃል አሉኝ፡፡ ይህንኑ ተቀብሎ ተጨዋቹ ሁሉ "ጐንደሬ" ይለኝ ጀመር፡፡ የቡድን አጋሮቼ በዚያ ሲጠሩኝ ደስ የሚላቸው ከሆነ ብዬ ተቀብዬዋለሁ፡፡ በስዊድን ስጫወት በአባቴ ስም ሳላህ ብለው ይጠሩኛል ፡፡ ምን ያህል
በክለብ ደረጃ መጫወት ስጀምር እናትና አባቴ ባወጡልኝ ስም ነበር የምጠራው፡፡ ድሮ ከሰፈር ጀምሮ ግን የወጣልኝ የቅጽል ስም ቤቢ ነው፡፡ አሁን ከፍተኛ ዕውቅና ካገኘሁ በኋላ ዋናው ስሜ ምንያህል መታወቅ ጀመረ እንጂ ብዙ ሰው ቤቢ እያለ ነው የሚጠራኝ፡፡ በቅጽል ስም መጠራራት ያዝናናል፡፡
ባለፈው ሰሞን እውቁ የአርሰናል አሰልጣኝ አርሴን ቬንገር ስለአፍሪካ ዋንጫ ተጠይቀው ባልተጠበቀ ሁኔታ ኢትዮጵያን ጠቅለዋል፡፡ በዘንድሮ የአፍሪካ ዋንጫ ኢትዮጵያ አለችበት፣ ግን ከኢትዮጵያ ቡድን የአምስት ተጨዋቾችን ስም ማንም አያውቅም ብለዋል፡፡ ከዚሁ የቬንገር አስተያየት ጋር ተያይዘው በወጡ ዘገባዎች፣ ኢትዮጵያ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ የምትሳትፈው ለዓለምና ለቬንገር ማንነቷን ለማሳወቅ ነው ብለዋል፡፡ እኔ በበኩሌ የቬንገር አስተያየት የብዙ አሰልጣኞች፣ የእግር ኳስ መልማዮችና የዝውውር ደላሎችን ቀልብ የሚስብ የዝውውር ጥሪ ይመስለኛል፡፡ እናንተስ?አዳነ
የቬንገር ንግግር ያለምክንያት አይደለም፡፡ ኢትዮጵያ የሚታወቅ ምንም ፕሮፌሽናል ተጨዋች ስለሌላት ይመስለናል፡፡ እኛ እግር ኳስ ሙያችን አድርገን የምንጫወት ፕሮፌሽናሎች ብንሆንም የምንወዳደርበት ፕሮፌሽናል ሊግ አለመኖሩ ዕውቅናችንን ቀንሶታል። ብዙውን ጊዜ ግን በእግር ኳስ ዙሪያ ያሉ ባለሙያዎች ለሚታወቁ ተጨዋቾችና ቡድኖች ትኩረት ከመስጠት ይልቅ አዲስ መጤ ለሆኑት ይጓጓሉ፡፡ ለዚህም ይመስለኛል ቬንገር ኢትዮጵያን በተለይ ሊጠቅሱ የቻሉት፡፡ እነ ጋና፣ ናይጀሪያ ይታወቃሉ ታይተዋል፡፡ ኢትዮጵያን ግን ማንም አያውቃትም፡፡ ቬንገር ብቻ ሳይሆኑ ብዙዎች እኛ ላይ ትኩረት ያደርጉብናል፡፡ ጌታነህ
በአፍሪካ ዋንጫ የሚሳተፉ አገራት እነ ናይጀሪያ፣ ጋና፣ እና ሌሎችም በአውሮፓ አሰልጣኞች ይታወቃሉ። ቬንገር ኢትዮጵያን የጠቀሱት ስለማውቃት እናያታለን ብለው ነው፡፡
አሰልጣኝ ሰውነት፣ በአፍሪካ ዋንጫ ራሳችንን እናስተዋውቃለን፣ እናሳያለን ብለው ለቬንገር ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ እስከ ሩብ ፍጻሜ የመድረስም ፍላጐት እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ በበኩላቸው፤ ዋንጫ ባታመጡ እንኳን ጥሩ ተጫውታችሁ አገራችሁን አስጠሩ ብለዋችኋል፡፡ ኢትዮጵያ ከዚህ አፍሪካ ዋንጫ ምን አይነት ውጤት ትጠብቅ?አዳነ
ያለንበት ምድብ ጠንካራ ነው፡፡ የኛ ቡድንም ግን ጠንካራ ነው፡፡ አንዳንድ ሚዲያዎች በተለይ የአገር ውስጥ ቡድናችንን የሚያነሳሳ ግምት ከመሰንዘር ይልቅ በጣም በሚያሳዝን ግምት የቡድናችንን አቅም የሚያወርድ አስተያየት መስጠታቸው ያሳፍራል፡፡ እኛ በቡድናችን ውጤታማነት የራሳችን እምነት እና እቅድ ቢኖረንም ሚዲያው ባለን አቅም ላይ የተሻለ ሞራልና መነሳሳት የሚፈጥር ግምት መሰንዘር ቢለምድ ጥሩ ነው፡፡
አንድ ምሳሌ እዚህ ጋ ልጥቀስልህ፡፡ የእንግሊዝ ብሔራዊ ቡድን በሚሳተፍባቸው የዓለም ዋንጫና የአውሮፓ ዋንጫ ውድድሮች በአገሪቱ ሚዲያ ከጅምሩ የሚሰጠው ግምት ተጋንኖ ነው የሚቀርበው፡፡ ውድድሮቹ ከመጀመራቸው በፊት በርካታ የእንግሊዝ ሚዲያዎች ቡድናቸውን በሚሰጡት ግምት ለዋንጫ ያጩታል። ተጨዋቾቹ የዓለም ምርጦች መሆናቸውን አድንቀው ይዘግባሉ፡፡ በእኛ አገር ሚዲያዎች ግን አነስተኛ ግምት የመስጠት አባዜ አለ፡፡ አላግባብ የማናናቅ እና የማውረድ ተግባር በተደጋጋሚ አጋጥሟል፡፡ እኛ በዘንድሮው የአፍሪካ ዋንጫ የምንሳትፈው ራሳችንንም አገራችንንም ወደተሻለ ደረጃ ከፍ ለማድረግ ነው፡፡ የመጀመሪያ ዙር አልፈን ጥሎ ማለፍ ውስጥ መግባት እንፈልጋለን፡፡ ጌታነህ
የመጀመሪያው ዓላማችን ከምድባችን ማለፍ ነው። ከዚያ በኋላ ያለውን የጥሎማለፍ ምዕራፍ በሂደት የመወጣት ፍላጐት ነው ያለኝ፡፡ አሉላ
የእኛ ስብስብ እዚህ ደረጃ መድረሱ አልተጠበቀም ነበር፡፡ ይህን ግምት ፉርሽ አድርጐ ለአፍሪካ ዋንጫ ደርሷል፡፡ እናም በ29ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በሚኖረን ተሳትፎ በተደጋጋሚ እንደተገለፀው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ክስተት ይሆናል፡፡ ብዙ እየተወራልን ነው። ዛምቢያ ሳይታሰብ ዋንጫ ወስዳለች፡፡ ማንም ወደ ውድድር ሲገባ ለማሸነፍ ነው ሌላ ትርጉም የለውም። እያንዳንዱን ጨዋታ ለክብር ነው የምንጫወተው። እርግጠኛ ነኝ በዚህ አፍሪካ ዋንጫ በኢትዮጵያ ቡድን ማንም ያልገመተው ውጠት ይመጣል፡፡ ሁሉም ቡድን ዋንጫ ለመውሰድ ያስባል፡፡ እኔ እያንዳንዱን ጨዋታ በትኩረት አድርገን ውጤታማ በመሆን ክስተት ሆነን ለመምጣት እንፈልጋለን፡፡
ዋንጫውን ከወዲሁ አናስብም፤ ከመጀመሪያ ጨዋታ ጀምሮ ትኩረታችን ተመሳሳይ ነው፡፡ ዩሱፍ
ጥሩ ቡድን አለን፡፡ በራሳችን ጨዋታ ማንንም ሳንፈራ በጥሩ ፉክክር እንሳተፋለን፡፡ ቡድናችን ከፍተኛ በራስ መተማመን አለው፡፡ ስለዚህ በማራኪ እግር ኳስ ተሳትፎ እናደርጋን፡፡