Administrator

Administrator

በፖለቲካ ግጭትና በገንዘብ እጥረት ሳቢያ የተጓተተው የዚምባብዌ ምርጫ፣ በደቡብ አፍሪካ ሸምጋይነትና በ100 ሚሊዮን ዶላር እርዳታ እርዳታ ቢታገዝም፣ እንደገና ከመራዘም አለመዳኑን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል። ለሰኔ ወር ታስቦ የነበረው ምርጫ፣ ወደ ሐምሌ፣ ከዚያም ወደ መጪው ጥቅምት ወር ተሸጋግሯል። በአልማዝ ማዕድን፣ በብረት ምርት፣ በእህል ኤክስፖርትና በሌሎች ጠንካራ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴዎች ትታወቅ የነበረችው አገር፣ እንጦሮጦስ የወረደችው በጥቂት አመታት ውስጥ ነው። ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ የሚመሩት መንግስት፣ የግለሰቦችን ንብረት እየወረሰና አለቅጥ ገንዘብ እያተመ፣ በ10 አመታት ውስጥ አገሪቱን የረሃብና የስራ አጥነት መናኸሪያ አድርጓቷል። የራሷ የገንዘብ ኖት የሌላትና ምርጫ ማካሄድ የማትችል የቀውስ መንደር የሆነችው ዚምባብዌ እንደአወዳደቋ በፍጥነት፣ ቶሎ ልታገግም ትችላለች ተብሎ አይታሰብም።

ዚምባብዌ፣ እንደ ሶማሊያ ወይም እንደ ኮንጎ በለየለት ጦርነት ውስጥ ሳትዘፈቅ፤ “በመንግስት ጥረት በአጭር ጊዜ ውስጥ የሾቀች አገር” በመሆኗ ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ለየት የምትል ትመስላለች። ለዚህም ነው፣ የአውሮፓ አገራትና አሜሪካ በሙጋቤ መንግስት ላይ፣ የተለያዩ ማዕቀቦችን የጣሉት። ነገር ግን፣ የመጠንና የደረጃ ጉዳይ ካልሆነ በቀር፣ ዚምባብዌ ከሌሎች የአፍሪካ አገራት ብዙም አትለይም። እጅግ ገዝፈውና ገንነው የሚታዩት የዚምባብዌ ሁለት ዋና ዋና ችግሮች…፣ ያው በሌሎች የአፍሪካ አገራትም ዘወትር የሚታዩ ችግሮች ናቸው። በአንድ በኩል፣ በፖለቲካ አፈናና ግጭት የምትናጥ አገር ነች - እንደ ብዙዎቹ የአፍሪካ አገራት። በሌላ በኩል ደግሞ የግል ቢዝነስን እንደ ጠላት የሚፈርጅ መንግስት፣ አለቅጥ ገንዘብ ማተምንና የውጭ እርዳታን የለመደ ነው - ይሄም በበርካታ የአፍሪካ አገራት የሚታይ ችግር ነው። የኬቶ ኢንስቲቱይት ጥናት እንደሚያመለክተው፣ የዚምባብዌ መንግስት በየአመቱ ብዙ የገንዘብ ኖት የማተም አባዜው እየተባባሰ የመጣው የዛሬ 15 አመት ገደማ ነው።

ከዚያም በፊት ቢሆን፣ ከልክ ባለፈ የገንዘብ ህትመት ሳቢያ “የዚምባብዌ ዶላር” ቀስ በቀስ ዋጋ እያጣ ነበር። በየአመቱ የሸቀጦች ዋጋ ከአስር እስከ ሃያ በመቶ እየናረ ቆይቷልና። በኢትዮጵያና በሌሎቹ የአፍሪካ አገራት በየጊዜው ከሚታየው የዋጋ ንረት አይለይም። እ.ኤ.አ ከ1998 በኋላ ግን፣ የገንዘብ ህትመቱ ይበልጥ እየጨመረ መጣ። እናም፣ ሃያ በመቶ የነበረው አመታዊ የዋጋ ንረት፣ ወደ 48% ዘለለ። መንግስት የገንዘብ ህትመቱን አደብ ሊያስገዛ ባለመፈለጉ፣ በቀጣዩ አመት የዋጋ ንረቱ ባሰበት - ወደ 60% ተጠጋ። እንደእብደት ሊቆጠር ይችላል። ግን፣ በአገራችንም ሚሊዬነሙ መባቻና የዛሬ ሁለት አመት የታየው የዋጋ ንረት፣ ስድሳ እና አርባ በመቶ ገደማ የደረሰ እንደነበር አስታውሱ። በእሳት መጫወት ይሉሃል ይሄ ነው! ለምን ቢባል፣ የገንዘብ ህትመት በጊዜ ካልተገታ፣ አብዛኛው ሰው በአገሬው ገንዘብ ላይ እምነት እያጣ፣ የዋጋ ንረት ከቁጥጥር ውጭ ይሆናል።

በዚምባብዌ ለሶስተኛ አመት ከሃምሳ በመቶ በላይ የሆነ የዋጋ ንረት ከተመዘገበ በኋላ ነው ነገር የተበላሸው። በ2001 የዋጋ ንረት ከእጥፍ ላይ በማሻቀቡ ኢኮኖሚው ተመሳቀለ። ከዚህ በኋላ መንግስት ሊቆጣጠረው አልቻለም። አዙሪት ውስጥ እንደመግባት ነው። በገንዘብ ህትመት የተነሳ ዋጋ ይንራል። በዋጋ ንረት ሳቢያ የመንግስት ወጪ ያሻቅባል። ወጪውን ለመሸፈን ገንዘብ ስለሚያትም የዋጋ ንረቱ ይባባሳል። በዚህ አዙሪት ውስጥ የገባው መንግስት፣ በዚያው አመት ለመጀመሪያ ጊዜ ባለ አምስት መቶ ኖት አሳተመ። በቀጣዩ አመት የዋጋ ንረት በእጥፍ ጨመረና 200% ደረሰ። መንግስት ባለ አንድ ሺ ኖት አሳተመ። የዋጋ ንረት ወደ 600% ተወረወረ። አንዴ ከቁጥጥር ውጭ ከሆነ በኋላ፣ እንደ ገና ወደ ጤንነት ለመመለስ ዳገት ነው። ያኔ፣ መንግስት ባለ 5ሺ፣ ከዚያ ባለ10ሺ፣ ከዚያም ባለ20ሺ ኖት አሳተመ - በሶስት ወራት ልዩነት። ትንሽ ቆይቶ ደግሞ ባለ ሃምሳ ሺ! የመቶ ሺ ኖት በታተመበት በ2006፣ የሸቀጦች ዋጋ በአመት ውስጥ በ12 እጥፍ ጨመረ። በ1998 ከነበረው የሸቀጦች ዋጋ ጋር ከተነፃፀረማ፣ የትየለሌ ነው። አንድ የዚምባብዌ ዶላር ይሸጥ የነበረው ክብሪት፣ ዋጋው ወደ ሰላሳ ሺ አሻቅቧል። በዚህ አላቆመም።

በቀጣዩ አመት መንግስት ባለ “ሁለት መቶ ሺ ኖት” ማሳተም ጀመረ። በወር ልዩነት የሩብ ሚሊዮን እና የግማሽ ሚሊዮን ኖቶች በገፍ ታተሙ። የዋጋ ንረት በአንድ አመት ውስጥ በስድስት መቶ እጥፍ ጨመረ። የዚምባብዌ መንግስት የ2008 አዲስ አመትን የተቀበለው ባለ ሚሊዮን ኖት በማሳተም ነው። ከዚያማ ተዉት። ወር ሳይሞላው ባለ አምስትና ባለ አስር ሚሊዮን ኖቶችን አምጥቶ አገሬው ላይ አራገፈው። ሁለት ወር ቆይቶ፣ በባለ 25 እና በባለ 50 ሚሊዮን ኖቶች አገር ምድሩን አጥለቀለቀው። አመቱ ሳይጋመስ፣ የመቶ ሚሊዮንና የአምስት መቶ ሚሊዮን ኖቶች ከታተሙ በኋላ፣ ባለ ቢሊዮን ኖት መጣ። አገር ጉድ አለ። የ25 እና የ50 ቢሊዮን ኖቶች እየታተሙ መሆናቸው አልታወቀም ነበር። የመቶ ቢሊዮን ኖት ደረሰ። በዚህ ወቅት “የዋጋ ንረት የት ደረሰ?” ብሎ ለማስላት መሞከር በጣም ከባድ ሆኗል - የሸቀጦች ዋጋ በየሰዓቱ ስለሚንር። የትሪሊዮን ኖቶች የመጡት በአዲስ አመት ነው - በ2009። በአመቱ የመጀመሪያው ወር ላይ፣ ዚምባብዌ የአለም ሪከርድ ሰበረች።

እስከዚያው ድረስ በአለማችን ከተመዘገቡት የዋጋ ንረት እብደቶች ሁሉ የባሰና፣ 14 ዜሮዎች የተደረደሩበት ባለ መቶ ትሪሊዮን ኖት አሳተመች። ግን ዋጋ የለውም። አንድ ሺ ያህል ባለ መቶ ትሪሊዮን ኖቶች ይዞ፣ አንዲት ዳቦ መግዛት አይቻልም። አብዛኛው ሰው፣ የአገሬውን ገንዘብ መጠቀም አቁሟል። በውጭ ምንዛሬ መገበያየት በአዋጅ ቢከለከልም፣ ሰዉ ሁሉ በዶላርና በዩሮ ብቻ የሚጠቀም ሆኗል። ምንም ማድረግ ስላልተቻለ፣ ከዚያን ጊዜ ወዲህ መንግስትም በዶላርና በዩሮ መጠቀም ጀመረ።

አገሪቱ ከዚያን ጊዜ ወዲህ የራሷ ገንዘብ የላትም። አዲስ አመትን በአዲስ የገንዘብ ህትመት መቀበል የለመደው የዚምባብዌ መንግስት፣ የእንጦሮጦስ ጉዞውን መቀጠል አልቻለም። እናም ዘንድሮ፣ በአዲስ አመት የመንግስት ካዝና ውስጥ የነበረው ገንዘብ 217 ዶላር ብቻ ነበር። ምርጫ ለማካሄድ መቶ ሚሊዮን ዶላር ከየት ይምጣ? እርዳታ ነዋ። አገሪቷ ግን በአልማዝ ማዕድን ከበለፀጉት የአለማችን አገራት መካከል አንዷ ነች። ነገር ግን፤ ኢኮኖሚን ለማቃወስ “የሚተጋ” መንግስት ባለበት አገር፣ መስራትና ማምረት ከባድ ነው። ከተመረተም፣ የዝርፊያና የሙስና ሲሳይ ነው የሚሆነው።

Cervical cancer… የማህጸን በር ካንሰር ...80% ያህል በታዳጊ አገሮች ይከሰታል

የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ፣የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር እና ጀርመን የሚገኘው ማርቲን ሉተር ዩኒቨርሲቲ በኢትዮጵያ የማህጸን በር ካንሰርን ለመከላከል የሚያስችል ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ በአዲስ አበባ ስብሰባ አካሂደዋል፡፡ እንደአውሮፓውያኑ የጊዜ ቀመር 10/4/2013 ማለትም ሚያዝያ 2/2005 በኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር የስብሰባ አዳራሽ በተካሄደው ስብሰባ በጋራ አብረው ለመስራት የታሰቡት ድርጅቶች ተወካዮችና ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስርም እንግዶች ተገኝተው ነበር፡፡ ዶ/ር ተናኘ ጸጥአርጌ ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር ስብሰባውን ሲከፍቱ እንደተናገሩት በኢትዮጵያ ከስነተዋልዶ ጤና ጋር በተያያዘ ለሴቶች ሞት በምክንያትነት ከሚጠቀሱት የማህጸን በር ካንሰር ይገኝበታል፡፡

ይህ በሽታ በብዙ ሴቶች ላይ የሚከሰትና በአስከፊነቱም በቀዳሚነት የተመዘገበ ነው፡፡ ማንኛዋም የግብረስጋ ግንኙነት የምትፈጽም ሴት በበሽታው ለመጠቃት እንደምትችል መረጃዎች እንደሚጠቁሙ ዶ/ር ተናኘ ተናግረዋል፡፡ ዶ/ር ካሳሁን ኪሮስ የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስትና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሜዲካል ፋኩልቲ በአንድ ወቅት እንደገለጹት የማህጸን ካንሰር አይነቱ ብዙ ሲሆን በአገራችን በብዛት የሚያጠቃውና ገዳይ የሆነው የማህጸን በር ካንሰር (Human Papiloma Virus) ሒዩማን ፓፒሎማ በተባለው ቫይረስ አማካኝነት የሚከሰተው ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ለማህጸን በር ካንሰር መከላከያ የሚሆኑ ሁለት አይነት ክትባቶች የተገኙ ሲሆን አንዱ Gardasil ሲሆን ሁለተኛው Cervarix የተሰኘው ነው፡፡ Gardasil K Human Papiloma Virus ለማህጸን በር ካንሰር መንስኤ ለሆነው መከላከያ ክትባት ሲሆን አራት የቫይረስ አይነቶችን ማለትም 16...18...6...እና 11 የተባሉትን የቫይረስ አይነቶች የሚከላከል ነው፡፡ በተመሳሳይም Cervarix የተባለው ክትባት 16...እና...18 የተባሉትን ቫይረሶችን ብቻ የሚከላከል የክትባት አይነት ነው፡፡ የማህጸን በር ካንሰር 70 ኀያህሉ የሚከሰተው በእነዚህ በ16 እና 18 በተባሉ የቫይረስ አይነቶች መሆኑ ተረጋግጦአል፡፡

በዓለማችን በየሁለት ደቂቃ አንድ ሴት በየሰአቱ ደግሞ ሰላሳ ሴቶች በማህጸን በር ካንሰር ምክንያት ለህልፈት ይዳረጋሉ፡፡ በዓለም አሀዝ መሰረት በየአመቱ እስከ ግማሽ ሚሊዮን ሴቶች የማህጸን በር ካንሰር ያላቸው መሆኑን በምርመራ የሚያረጋግጡ ሲሆን ከእነዚህም እስከ ሁለት መቶ ሰባ አምስት ሺህ የሚሆኑት በዚሁ ህመም ምክንያት ሕይወታቸው ያልፋል፡፡ ዶ/ር ተናኝ ጸጥአርጌ ከኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር እንደገለጹት በብሄራዊ ደረጃ በየአመቱ ወደ 7619/ ሰባት ሺህ ስድስት መቶ አስራ ዘጠኝ ሴቶች በማህጸን በር ካንሰር ሊያዙ እንደሚችሉና ከነዚህም ወደ 6081/ ስድስት ሺህ ሰማንያ አንድ የሚሆኑት ለህልፈት እንደሚዳረጉ ይገመታል፡፡ ይህ ቁጥር የሚያሳየው ምን ያክል ታማሚዎች እንዳሉና የሞት ቁጥሩም ቀላል እንዳልሆነ ሲሆን በተያያዠነትም ለጉዳዩ የተሰጠው ትኩረት ምን ያህል እንደሆነ እንዲሁም አገልግሎቱ መስፋፋት እንዳለበትም የሚጠቁም ነው፡፡

የኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስር በብሕራዊ ደረጃ ወደ 118/የሚሆኑ የጤና ተቋማት የማህጸን በር ካንሰርን በሚመለከት ትኩረት ሰጥተው እንዲሰሩ የሚያስችል አሰራር በመዘርጋት ላይ ነው፡፡ ስለዚህም ይህንን በሽታ ለመከላከል በቂ የሆነ የህክምና አገልግሎት መሰጠት በምእተ አመቱ የልማት ግብ ከታቀዱት መካከል የእናቶችን ሞት ለመቀነስ ይረዳል፡፡ እስከአሁን ባለው አሰራር ለ2015/ የታቀደውን የልማት ግብ ለማሳካት ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ እና ውጤት የሚያስመዘግቡ ስራዎች እየታዩ ቢሆንም አሁንም ገና ብዙ መሰራት እንዳለበት ከሚጠቁሙት እውነታዎች መ..ከል የማህጸን በር ካንሰር ይኝበታል፡፡ ይህም በብሕራዊ ደረጃ ከታቀደው የስነተዋልዶ አካላት ጤና አጠበባበቅ ጋር የሚገናኝ ነው ብለዋል ዶ/ር ተናኘ፡፡ ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት በአ.አ ዩኒቨርሲቲ ሕክምና ፋክልቲ መምህር እና የኢሶግ ፕሬዝዳንት በትብብር መስራትን በሚመለከት በሰጡት ማብራሪያ .. ...እንደሚታወቀው በአብዛኛው ትኩረት የሚሰጠው አጣዳፊ ለሆኑት እና ተላላፊ በሽታዎች ቢሆንም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ይህ አዝማሚያ እየተለወጠ ሌሎች ከሰው ሰው በቀላሉ የማይተላለፉ ነገር ግን ሕይወትን አደጋ ላይ የሚጥሉ የጤና ችግሮችም ትኩረት እያገኙ በመምጣት ላይ ናቸው፡፡

ለምሳሌ..የውስጥ አካላት ሕመሞች...የደም ግፊት...የስኩዋር ሕመም የመሳሰሉት ከሰው ሰው በመተላለፍ ጉዳት የማያስከትሉ ቢሆንም ሰዎችን ግን ጤናቸውን የሚያቃውሱ በመሆኑ በአለም አቀፍ ደረጃ አትኩሮትን ያገኙ ናቸው፡፡ በዚሁ ረገድም ከስነተዋልዶ አካላት ጋር ተያይዘው የሚገኙ የተለያዩ የካንሰር አይነቶችን በሚመለከት የበለጠ ግንዛቤ የሚገኝበት የችግሩም ስፋት የሚታወቅባቸው መድረኮች እየተፈጠሩ ነው፡፡ የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር አባላት አብዛኞቹ በቀጥታ ከጽንስና ማህጸን ሕክምና ጋር የተያያዘ የህክምና አገልግሎት የሚሰጡ እንደመሆናቸው ታማሚዎችን በህክምናው አገልግሎት የመርዳት ስራ ይሰራሉ፡፡ በዚህም እንደሚታየው አብዛኞቹ የማህጸን በር ካንሰር ታማሚዎች ወደህክምናው የሚመጡት በሽታው ስር ከሰደደና ከተሰራጨ በሁዋላ በመሆኑ በቀላሉ ለማከምና ለማዳን እጅግ ፈታኝ ሁኔታዎች ይገጥማሉ፡፡ ስለዚህ ይህንን ሁኔታ ለመለወጥ ምን ማድረግ ያስፈልጋል የሚለውን ለመነጋገር የተፈጠረው የምክክር መድረክወደ ሶስት ነገሮችን ማድረግ እንደሚቻል አሳይቶአል፡፡

ግንዛቤ የማስጨበጥ ስራ መስራት ... ሴቶች በችግሩ ስር በሰደደ እና በከፋ ሁኔታ ከመጠቃታቸው በፊት ሊታከሙ በሚችሉበት የህክምና ተቋም በመሄድ ሕክምና እንዲያደርጉ ያስችላል የሚል ግምት አለ፡፡ የችግሩን ስፋትና ጥልቀት ማወቅና የዚያኑ ያህል ተመጣጣኝ የሆኑ እንቅስቃሴ ዎችን ማድረግ አስፈላጊ በመሆኑ አንዳንድ የዳሰሳ ጥናቶችን ማድረግ፣ይህም የሚሰሩ ስራዎች በትክክለኛ መረጃ ላይ የተመሰረተ ከሆነ የተጀመረውን ፣ መሰራት የሚገባውንና ከአመታት በሁወላ ሊደረስበት የሚገባውን ደረጃ ለማወቅ ይረዳል፡፡ ቅድመ ካንሰር ሁኔታውን አስቀድሞውኑም ማወቅ የሚቻልበት የህክምና አሰራሮች ስላሉ ይህንን አገልግሎት በቀላሉና በስፋት እንዴት ማዳረስ ይቻላል የሚለውን ስብሰባው ተመልክቶአል፡፡ ለዚህም ተቋሞችን በሰለጠነ የሰው ኃይል እና በተገቢው መሳሪያ ማጠናከር እና አስፈላጊው ግብአት የሚገኝበትን ሁኔታ ስብሰባው ተነጋግሮአል፡፡ የካንሰር ሕክምና እስከአሁን የሚሰጠው ውስን በሆኑ የህክምና ተቋማት በተለይም በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ሲሆን ነገር ግን የሆስፒታሉ አቅም ውስን በመሆኑ ታካሚዎች በጣም ለረጅም ጊዜ ህክምናውን ለማግኘት ወረፋ የሚጠብቁበት ሁኔታ ይታያል፡፡ ይህንን ለውጦ ተደራሽነትን ለማስፋት እንዴት ይቻላል የሚለው መልስ እንዲያገኝ ክህሎትን የማሳደግና ግብአትን የማሟላት ስራ መስራት አስፈላጊ መሆኑ ተጠቁሞአል፡፡

ይህ እቅድ ከተሳካ በሚቀጥሉት ሁለት አመታት ውስጥ ጠንካራ ስራዎችን መስራት ይቻላል ተብሎ ይታሰባል፡፡ ይህ እሳቤ እውን ከሆነ በሁዋላም የማህጸን በር ካንሰርን የመከላከል ስራ በፕሮጀክት ተይዞ የሚቀጥል ሳይሆን ከተወሰኑ የጊዜ ሂደቶች በሁዋላ እንደማንኛውም መሰረታዊ የጤና ሁኔታ ተይዞ በአገር አቀፍ ደረጃ በተሙዋላ አገልግሎቱን መስጠት ይቻላል የሚል እምነት አለ፡፡ የካንሰር ህክምና በሶስት ደረጃ ተመጣጥኖ የሚሰጥ ነው፡፡ እሱም የጨረር ፣የቀዶ ሕክምና እና በመድሀኒት የሚሰጥ በመሆኑ ከፍተኛ ወጪን የሚጠይቅ ነው፡፡ አሰጣጡም ለየትኛው ታማሚ ምን አይነት ሕክምና ያስፈልገዋል የሚለው በምርመራ አማካኝነት የሚወሰን ሲሆን ወጪው ለምርመራ የሚረዱ መሳሪያዎችን ከማሟላት አንጻር ብቻ ሳይሆን የሙያተኞች እና የሚወሰዱ መድሀኒቶችን ጭምር ያካትታል፡፡ የምርመራ መሳሪያዎችን ሁኔታ ስንመለከት ደግሞ እጅግ ዘመናዊ የሆኑ መሳሪያዎች በአለም ገበያ ላይ የሚገኙ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ዋጋቸው ተመጣጣኝ የሆነ ብዙ ሰዎችን ለመርዳት የሚያስችሉም አሉ፡፡ ስለዚህ በከፍተኛ ደረጃ የሚገኘውን የክኖሎጂ ውጤት የምንጠብቅ ከሆነ አቅምም ስለማይፈቅድ ተጠቃሚ የሚሆኑትም ውስን ተቋማት ናቸው፡፡

ዝቅተኛ ወጪ የሚያስወጡ አማራጭ የምርመራ ዘዴዎችን የምንጠቀም ከሆነ ግን አሰራሩን በስፋት እስከጤና ጣቢያ ድረስ መዘርጋት የሚያስችል ሁኔታ ይፈጠራል፡፡ በአገራችን ያለውን የእናቶች ሞት መጠን ለመቀነስ እንዲያስችል አገልግሎቱን በስፋት ማዳረስ አማራጭ የሌለው አሰራር መሆኑን አምኖ በተመጣጣኝ ዋጋ በስፋት ሊዳረስ የሚችለውን መሳሪያ እና ግብአት ወደሀገር በማስገባት የብዙ ሴቶችን ሕይወት ማትረፍ ተገቢ ነው በሚል ከስምምነት የተደረሰበት ነበር የጋራ ምክክሩ ብለዋል ዶ/ር ይርጉ ገ/ሕይወት የኢሶግ ፕሬዝዳንት፡፡ ማንኛዋም ሴት በተለይም እድሜዋ ከሰላሳ አመት በላይ ከሆነ ቢቻል በየአመቱ ባይቻል በየሶስት አመቱ አለበለዚያም በየአምስት አመቱ የቅድመ ካንሰር ምርመራ ብታደርግ ካንሰርን አስቀድሞ መከላከል ይቻላል፡፡ መጥፎ ጠረን ያለው የማህጸን ፈሳሽ ከግብረስጋ ግንኙነት በሁዋላ ወይንም ብልትን በማጽዳት ወቅት እንዲሁም ሰውነት በመንካት ወቅት ደም መፍሰስ ካሳየ ወዲያውኑ ወደሐኪም ሄዶ መፍትሔ ማግኘት ይቻላል፡፡

ሀዋስ ፋሚሊ ፊልም፤ “የራስ አሽከር” የተሰኘ አዲስ የቤተሰብ ልብ ሰቃይ ፊልም በነገው እለት በ8,፣10 እና 12 እንደሚያስመርቅ አስታወቀ፡፡ በአዲስ አበባና በግል ሲኒማ ቤቶች የሚመረቀውን የ100 ደቂቃ ፊልም የፃፈው ዘካርያስ ካሳ ነው፡፡ ሰርቶ ለማጠናቀቅ ሃያ ዘጠኝ ወራት የፈጀው ፊልም፤ ቀረፃ የተከናወነው በአዲስ አበባ፣ በደብረዘይትና በደቡብ ክልል እንደሆነ ታውቋል፡፡ በፊልሙ ላይ ሽመልስ አበራ (ጆሮ)፣ ዝናህብዙ ፀጋዬ፣ ቶማስ ቶራ፣ ዳንኤል ሙሉነህ፣ እሱባለው ተስፋዬ፣ ትዕግስት ዋሲሁን፣ ወንድወሰን ብርሃኑ (ዶክሌ)፣ አንዱአለም ሽፈራው እና ሌሎችም ተውነዋል፡፡

ድምፃዊ ዮሴፍ ገብሬ (ጆሲ) አዲስ የቴሌቪዥን ቶክ ሾው ሊጀምር መሆኑን አስታወቀ፡፡ በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ሰርቪስ (EBS) የሚጀመረው የቴሌቪዥን ቶክ ሾው Jossy in z House የሚል ርእስ ያለው ሲሆን ዝግጅቱ በፋሽን እና ስነጥበብ ላይ ያተኩራል፡፡ የነገ ሳምንት በእለተ ትንሳኤ የሚጀመረው ዝግጅት ዘወትር እሁድ ምሽት ከሁለት ሰዓት ጀምሮ ለአንድ ሰዓት የሚታይ ሲሆን ሐሙስ ከምሽቱ 4 ሰዓት ይደገማል፡፡

በዶ/ር ግርማ ግዛው የተዘጋጁና በሥራ ፈጠራ ላይ ያተኮሩ ሁለት መፃህፍት በነገው እለት በፑሽኪን አዳራሽ ከረፋዱ 4 ሰዓት ላይ እንደሚመረቁ አዘጋጁ አስታወቁ፡፡ መፃህፍቱ፤ “ሥራ ፈጠራ፣ ጥቃቅን አነስተኛና መካከለኛ የንግድ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ሕግ እይታ” እና “ሥራ ፈጠራ፣ ንግድ እና የንግድ ሥነምግባር” በሚሉ አርእስት የተፃፉ ናቸው፡፡

ሥነ ጽሑፍን፣ ነፃ የሀሳብ መንሸራሸርንና የንባብ ባሕልን በማጐልበት የሚንቀሳቀሰው ፔን ኢትዮጵያ፤ ሁለተኛውን የፀሐፍት ጉባዔ ዛሬ በጣሊያን የባሕል ማዕከል ሊያካሂድ ነው፡፡
የጉባኤው ጭብጥ “የትርጉም ሚና ለኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ እድገት” በሚል ሲሆን፤ ምሁራን ጥናታዊ ጽሑፎቻቸውን እንደሚያቀርቡና ውይይት እንደሚደረግባቸው ተገልጿል፡፡
በጉባኤው ላይ የፔን አባላት የሆኑ ገጣሚያን፣ ፀሐፊ ተውኔቶች፣ ልብወለድ ፀሐፊዎች፣ ጋዜጠኞችና ሌሎች የሥነ ጽሑፍና የሚዲያ ቤተሰቦች ታዳሚ ሲሆኑ የኖርዌይና የጣሊያን ፔን ፕሬዚዳንቶችን በእንግድነት ይገኛሉ፡፡

 

Saturday, 27 April 2013 11:51

የግጥም ጥግ

ገና ከጅምሩ
በቤት አራሥነት ሸክም … በአዲስ ኑሮ
አሐዱ ብዬ
የራስ ማስተዳደር ማተብ ሳጠልቅ … ከወላጅ እትብት
ተገንጥዬ
ሲሟሽ ሲሟሽ ሲታሰስ … ሲጋገር የመኖር እንጎቻዬ
በቆራስማ ማጥንት ታጥና … ማጠንሰስ ስትጀምር ገንቦዬ
ኑሮን አልፋ ብዬ ኑሮን በስመአብ ብዬ
ኑሮ ኪራራይሶን
ገና አንዲት ዶቃ ላማትብ ስቆጥር
ምነው ያደርገኛል እንደመፍዘዝ ነገር
እንደመቆናጠር
ተስፋን መቁረጥ አይሉት ወይ ተስፋን ማጠናከር
መበራታት አይሉት ወይ መደነጋገር
ብቻ የሆነ ስሜት ብቻ የሆነ ነገር
እኩል አይሉት ሠናይ ደስታ አይሉት ሥቃይ
ብቻ የሆነ ሥሜት ግልጽ ያልሆነ ጉዳይ

***

ሰሙ ዝቅ ወርቁ ርዝቅ
በቀመር ተሰልቶ፣
በዋጋ ተዋዝቶ፣
በሰም ቢታሸግም
ያለ ወርቅ እሺ አይልም፡፡
የዛሬ ጨረታ ኩሩ ነው ቀብራራ፤
ራሱን ይኮፍሳል፤
በታክቲክ ዝቅ ብሎ፣
በቴክኒክ ከፍ ይላል፡፡
(“ከጃርት ወደ ጃርት” ከሚለው
የካሣሁን ከበደ
የግጥሞች እና ወጐች መድበል የተወሰደ - 2000 ዓ.ም)

 

 

አንድ ብዙ አማካሪ ያላቸው ንጉሥ፤ ሁሉም ባለሟሎቻቸው በተሰበሰቡበት አንድ ጥያቄ ጠየቁ፡፡ “የመጀመሪያው ጥያቄዬ”፣ አሉ ንጉሡ፡፡ “ከዚህ እስከሰማይ ምን ያህል ርቀት እንዳለው የሚያውቅ ይንገረኝ?” አሉ፡፡ ሁለተኛው ጥያቄዬ፤ “እኔ ብሸጥ ምን ያህል የማወጣ ይመስላችኋል?” “አስበን እንምጣ ንጉሥ ሆይ!” ብለው ባለሟሎቹ ሄዱ፡፡ ከዚያም፤ አንደኛው - ኮከብ ቆጣሪዎችን እንጠይቅ አለ ሁለተኛው - ኮከብ ቆጣሪዎች ዕጣ - ፈንታ እንጂ ኪሎ ሜትር አያውቁም፡፡ ይልቅ ደብተራዎችን እንጥራና የሚደግሙትን ደግመው የሚገለጥላቸውን ይንገሩን፡፡ ሦስተኛው - ደብተራዎችም ቢሆኑ ስለአጋንንት ትብትብ መፍቻ፣ ስለመናፍስት እንቅስቃሴ እንጂ ስለምድር - ሰማይ ርቀት የሚደግሙት የላቸውም፡፡

አራተኛው - እንግዲያው አዋቂ እንጠይቅ አምስተኛው - ጠንቋይ ለራሱ አያውቅም ባካችሁ፤ ይህንን ያንን እያነሱና እየጣሉ ሲከራከሩ፤ ከአቅራቢያቸው የሚገኝ አንድ ደበሎ - ለባሽ ያዳምጣቸው ኖሮ፤ “አባቶቼ፤ ይሄ የምትነጋገሩበት ነገር እንዲህ የሚያሟግትና ሊቅና ደብተራ የሚያፋልግ ጉዳይ አይደለም” አላቸው፡፡ ይሄኔ አንደኛው፤ “ታዲያ ምን እናድርግ ትላለህ በእኛ ዕውቀት ደረጃ የምንፈታው ባይሆንልን እኮ ነው፡፡” የቆሎ ተማሪውም፤ “እኔ መልሱን ልሰጣቸው እችላለሁ፡፡ ንጉሡ ፊት አቅርቡኝ” አላቸው፡፡ አማካሪዎቹ ጥቂት ካቅማሙ በኋላ፤ በቃ እንውሰደውና ይናገር ብለው ተስማሙ፡፡ ንጉሡ ዘንድ ቀርበውም፤ “ንጉሥ ሆይ! ንጉሥ ለጠየቁት መልስ መስጠት እችላለሁ የሚል ሰው ይዘን መጥተናል” ንጉሥ - “ይቅረባ እንየው!” የቆሎ ተማሪው ሲቀርብ ንጉሡ ተገርመው፤ “ይሄ ደበሎ - ለባሽ ነው የረባ መልስ ይሰጣል ብላችሁ ያመናችሁት?” አንደኛው - “አዎ ንጉሥ ሆይ!” ንጉሥ - “ጥያቄዬ፤ ‘ከመሬት እስከ ሰማይ ምን ያህል ይርቃል? እኔ ብሸጥስ ምን ያህል አወጣለሁ?’ የሚል ነው፡፡

“ የቆሎ ተማሪውም፤ “ንጉሥ ሆይ! ከዚህ እስከ ሰማይ 1000 ኪ.ሜ ይሆናል፡፡ አይበለውና እርሶ ቢሸጡ 29 ብር ያወጣሉ፡፡” ንጉሥ - እኮ አስረዳና! ቆሎ ተማሪው - “ከመሬት እስከሰማይ ያለውን ለመለካት ስለማይችሉ ነው 1000 ኪ.ሜ ያልኩት 29 ብር ያልኩዎት ደግሞ እየሱስ የተሸጠው 30 ብር በመሆኑ ነው፡፡ እርሶ ከዚያ ያንሳሉ፡፡ ስለዚህም ቢያወጡ ቢያወጡ በአንድ ያንሳሉ ብዬ ነው፡፡ ንጉሡ በመልሱ ተደስተው፣ አመስግነው ሸለሙት፡፡ * * * ስመ-ጥር አማካሪዎች የማይሰነዝሩዋቸው፣ ተራ የሚመስሉ አስተዋይ ሰዎች ግን ሳይጠራጠሩ የሚሰጡት ፋይዳ ያለው አስተሳሰብ፤ አገር ያድናል፡፡ የበታች ሆነው ታስበው፣ ታላቅ ሃሳብ ሊያቀርቡ የሚችሉ ሰዎችን በፋኖስ መፈለግ ያስፈልጋል፡፡ ለመፈለግ ደግሞ “ከእኔ ውጪም ለአገር አሳቢ ሊኖር ይችላል” ብሎ ማመን ተገቢ ነው፡፡ “ትኬት አልገዛም፤ ዝም ብዬ ባቡሩ ላይ እሳፈራለሁ” በሚል ሚንግዌይ ስለድፍረት ነግሮናል። ወይ የባቡሩ ሸፍተራን ይታለላል፡፡

ወይ አይመጣም፡፡ ወይ እንደራደራለን። አለበለዚያ እወርዳለሁ፤ ብለን የምንጓዘው ጉዞ፤ ለግዴለሽ ዕቅድ - አልባነታችን መገለጫ ይሆነናል፡፡ ያለዕውቀት ባቡሩ ላይ መሳፈር ወይ የብልጠት፣ ወይ አይነቃብኝም ብሎ የማሰብ ወይም ሌላውን የመናቅ አሊያም ተደባልቆ የመጓዝ ሁኔታ፤ እነሆ ዛሬ ከዘመናት በኋላ ፈጣን ነው ባቡሩን እንድንዘፍን ያደርገናል፡፡ ሳርኮክ የተባለው ፈላስፋ፤ በፍልሚያ የሚያምኑ አካላት፤ በጦርነት ሌሎቹን ድል ካደረጉ በኋላ፤ ‘ጠላት ካጣን እርስ በርስ ይዋጣልና’ የሚል ደረጃ ይደርሳሉ” የሚለንን ልብ እንበል፡፡ ሁልጊዜ የአገሬ እድገት፤ በኪራይ ሰብሳቢዎች ላይ ያገኘሁት ድል ነው! ምርጫው ያለሳንካ በመካሄዱ ነው! ፀረ - ህዝብና ፀረ - ህገመንግሥት አመራሮችን በማስወገዳችን ነው! ወዘተ… ከሚለው ባሻገር፣ ከሣጥኑ ወጣ ብለን ለማሰብ እንሞክር፡፡

ችግሮችን ወደህዝብ ማድረስ የሀቀኛ ዜጐች ግዴታ ነው!! ሆኖም ያለንበት ሁኔታ አንድ ክስተትን አጉልቶ እያሳየን ነው፡- የታፈኑ የሚመስሉ ጉዳዮች ነበሩንን? የሚል፡፡ የጤናማ አመለካከት ጥያቄ ነው፡፡ በህዝብና በአገር ላይ ክፉ ድርጊት ሲፈፀም እርምጃ ሳይወስዱ እጁን አጣጥፎ መቀመጥ አደገኛ እንደሆነ ሁሉ፤ እርምጃንም በስሜታዊነት ወይም በመካር አሳሳቾች ግፊት ከመውሰድ መቆጠብ ያባት ነው! ሰሞኑን “መልካም አስተዳደር በዘመቻ የሚፈታ ችግር አይደለም” የተባለው አስገራሚ አረፍተነገርና ዕውነታ፤ “የጠፋው በግ ተገኘ” የሚያሰኝ ነው፡፡ መልካም አስተዳደር፣ በሙያ በበሳል - ጥበብ (wisdom)፣ የህዝብ ጥቅም - ተኮር በሆነ መልክ ይቃኝ፤ ተብሎ አያሌ ጊዜ ተነግሮ ዛሬ ይፋ መሆኑ አስደሳች ነው፡፡

ዘመቻ በየአቅጣጫው ሊፈተሽ ሊመረመር ይገባል - ለሀገርና ለህዝብ ጥቅም ሲባል፡፡ ነኒውሪን ቤቫን የተባለው ፖለቲከኛ ስለቸርችል እንደጻፈው፤ ከዓለም ጋር ያለ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፣ የጐረቤት ሀገሮች ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፣ እርስ በርስ ያለ ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት፤ ሲላላ፤ በ20ኛው ክ/ዘመን ያለው ዲፕሎማት የ18ኛው ክ/ዘመን ቋንቋ የሚናገር ይሆናል፡፡ አስቸጋሪ ሁኔታ በገጠመው ቁጥር ግን “ተኳሽ - ጀልባ ላኩ” ከማለት አይቆጠብም! ይላል፡፡ ቀልብን ገዝቶ፣ አዕምሮን አትብቶ አገርን ማስተዋል የታላቅ መሪ ጥበብ ነው፡፡ መሪ፤ “ንፁህ ወርቅ እሳት አይፈራም!” የሚለውን አልሰማ ብሎ ከተዘናጋና እሳቱ እየበላው መሳቅ መጫወት ከሆነ ሥራው፤ ስለሀገራችን እርግጠኛ መሆን አንችልም፡፡ “ሸማኔ ውሃ ሲወስደው፣ እስካሁን አንድ እሰድ ነበር፤ አለ” ማለት ይሄው ነው!!

  • 1 የአቶ መለስ ዜናዊ ምትክ መሆናቸውን ለማስመስከር የሞከሩበት ነው ግዙፎቹ እቅዶች (ለምሳሌ የባቡር ፕሮጀክት) መጓተታቸውንና የገንዘብ ችግርን በሚመለከት፣ እንዲሁም በቤኒሻንጉል የተፈናቀሉ ሰዎች ዙሪያ ትችት አዘል ጥያቄ ቀርቦላቸዋል። ጠ/ሚ ኃይለማርያም ለፓርላማው የሰጡት ምላሽ፣ የአቶ መለስን ዘዴ የተከተለ ነው - “መንግስት ላይ በተሰነዘረው ትችት ላይ የባሰ ትችት የመጨመር ዘዴ”
  • 2. የማይሳካ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ አጣብቂኝ ሆኖባቸዋል ግዙፎቹ የግድብ፣ የባቡር፣ የኢንዱስትሪ. የኤክስፖርት እቅዶች፣ እንዲሁም የእህል ምርት ለማሳደግና ስራ አጥነትን ለማቃለል የወጡ እቅዶች የማይሳኩ መሆናቸውን ከምር አምነው ለመቀበል አልደፈሩም። እቅዶቹ “በተያዘላቸው ጊዜ እየተተገበሩ ናቸው” እያሉ በተደጋጋሚ ይናገራሉ። ግን ደግሞ “የመቀነስ አዝማሚያ ታይቷል” ይላሉ።

እውነት ለመናገር ኢህአዴግ በ”ስሜት” ተነሳስቶ በ2002 ዓ.ም መጨረሻ ላይ ያዘጋጀው “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ” አልሳካ ያለው በጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ ድክመት አይደለም። እቅዱ እንደማይሳካ በተግባር የታየው በመጀመሪያው አመት በ2003 ዓ.ም ነው። አምና ደግሞ፤ የእቅዱ ውድቀት አፍጥጦ ወጣ። በዚህ በዚህ፣ አቶ ኃይለማርያም ከሌሎች የኢህአዴግ መሪዎች የተለየ ተጠያቂነት ሊጫንባቸው አይገባም። በአብዛኛው የመንግስት ፕሮጀክቶች በማስፋፋት የአገሪቱን ኢኮኖሚ በአምስት አመት ውስጥ በእጥፍ ለማሳደግ ታስቦ እቅድ መውጣቱ ነው ዋነኛው ጥፋት። በመንግስት ፕሮጀክቶችና ኮርፖሬሽኖች አማካኝነት አገር ሊያድግ እንደማይችል በደርግ ዘመን በደንብ ታይቷልኮ።

የኢህአዴግ “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድም” ከውድቀት ሊያመልጥ የማይችለው፤ እንደ ደርግ እቅድ የግል ኢንቨስትመንትንና የግል ጥረትን የሚያጣጥ በመሆኑ ነው - በአጭሩ በአቶ ሃይለማርያም ድክመት አይደለም የኢህአዴግ እቅድ ሳይሳካ የሚቀረው። ይልቅስ፣ ጠ/ሚ ኃይለማርያምን ተጠያቂ የምናደርጋቸው፤ የአምስት አመቱ እቅድ እንደማይሳካ እየታወቀ፤ “እየተሳካ ነው፤ እንደታቀደው እየተሰራ ነው” ብለው ሊያድበሰብሱ ከሞከሩ ነው። በእርግጥ፤ እቅዱ እየተሳካ አለመሆኑን ሙሉ ለሙሉ አልካዱም። የእርሻ ምርት እንደታሰበው አላደገም ብለዋል። ኤክስፖርትም እንዲሁ።

“የጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ምርታማነት”ም የተወራለት ያህል እንዳልሆነ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ጠቅሰዋል። እንዲያም ሆኖ፤ እቅዱን አለመሳካት ሙሉ ለሙሉ ባይክዱም፤ ሙሉ ለሙሉም አምነው አልተቀበሉም። “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ”፤ ከሞላ ጎደል በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ እየተተገበረ እንደሆነ ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተደጋጋሚ የገለፁት። ለመሆኑ የትኛው እቅድ ነው፤ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ እየተከናወነ የሚገኘው? ካሁን በፊት እንደጠቀስኩት፣ ትልቅ ትኩረት የተሰጠው የህዳሴ ግድብ ግንባታ እንኳ በእቅዱ መሰረት እየተከናወነ አይደለም። በጣም ተጓቷል። በአምስት አመት ውስጥ ግንባታው ይጠናቀቃል ነበር የተባለው። ግን በሁለት አመት ውስጥ የተከናወነው ስራ፣ 18 በመቶ ብቻ ነው። በዚህ ስሌትም፣ ግንባታው 11 አመት ሊፈጅ ይችላል። “የግልገል ጊቤ 3” ግንባታም እንዲሁ፤ በእቅዱ መሰረት ሊሄድ አልቻለም። በ1998 ዓ.ም የተጀመረው የግልገል ጊቤ 3 ሃይል ማመንጫ፣ የዛሬ ሁለት አመት ግንባታው ተጠናቅቆ ወደ ስራ እንዲገባ ታቅዶ ነበር። አልተሳካም።

እቅዱ ተከልሶ፣ የግንባታ ማጠናቀቂያ ጊዜው ወደ ዘንድሮ ተራዘመ። ግን እንኳን ዘንድሮ በሚቀጥለው አመትም አይጠናቀቅም። ግንባታው ገና 71% ላይ ነው። ቢያንስ ተጨማሪ ሶስት አመት ሳያስፈልገው አይቀርም። እናም በ2002 ዓ.ም ወደ ሁለት ሺ ሜጋ ዋት ገደማ የነበረው የኤሌክትሪክ ሃይል የማመንጨት አቅም፣ በ50 በመቶ እንዲያድግና ዘንድሮ ሶስት ሺ ሜጋ ዋት እንዲደርስ የወጣው እቅድ አልተሳካም። እዚያው ከነበረበት ደረጃ ፈቅ አላለም። ከሁሉም የላቀ ትኩረት የተሰጣቸው ግድቦች፣ በተያዘላቸው እቅድ ሊከናወኑ ካልቻሉ፣ ሌሎቹ እቅዶች ምን ያህል እንደሚጓተቱ አስቡት። በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ የተጠቀሱት ግዙፍ የሳሙናና የወረቀት ፋብሪካዎችም ድምፃቸው የለም። ዋነኛ የእድገት መሰረት ይሆናሉ ተብለው በመንግስት በጀት የተመደበላቸው አነስተኛና ጥቃቅን አምራች ተቋማትስ? ከቁጥር የሚገባ ለውጥ አልተመዘገበም። ፈፅሞ የእድገት ምልክት አልታየባቸውም። እንዲያውም፣ ከሌሎች የኢኮኖሚ ዘርፎች ጋር ሲነፃፀሩ፣ አነስተኛና ጥቃቅን አምራች ተቋማት ወደ ኋላ እየቀሩ መሆናቸውን የገንዘብና ኢኮኖሚ ልማት ሚኒስቴር መረጃ ያመለክታል። ለነገሩ፣ በኢህአዴግ ጉባኤ ላይም በግልፅ ተጠቅሷል።

የአምናው የእርሻ ምርት እድገትም እንዲሁ የእቅዱን ግማሽ አያክልም። በአማካይ በነፍስ ወከፍ ስሌት፣ የእርሻ ምርት በ6 በመቶ እንዲያድግ ቢታቀድም፣ በተግባር ግን ከ2.5 በመቶ ያለፈ እድገት አልተገኘም። ብዙ የተወራላቸው አዳዲስ 10 የስኳር ፋብሪካዎችም ገና ብቅ አላሉም። ከ8 አመት በፊት የተጀመሩ ነባር የስኳር ፋብሪካ ፕሮጀክቶች እንኳ፣ በወጉ ሊጠናቀቁ አልቻሉም። የስኳር ምርት በሶስት እጥፍ አድጎ ዘንድሮ 10 ሚሊዮን ኩንታል ገደማ ይደርሳል ተብሎ ነበር - በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ። እህስ? የዛሬ አራት አመት ከነበረበት ደረጃ ትንሽ እንኳ ፎቀቅ አላለም። እንዲያውም ወደ ታች ወርዷል፤ ከ3 ሚሊዮን ኩንታል በታች ሆኗል። ከአገር ውስጥ ፍጆታ የሚበልጥ ስኳር ተመርቶ፣ ዘንድሮ በኤክስፖርት ወደ ሁለት ቢሊዮን ብር ገደማ ገቢ ይገኝበታል ተብሎ ነበር። ጠብ ያለ ነገር የለም። እንዲያውም የአገር ውስጥ ፍጆታን ለማሟላት ከውጭ ስኳር ለማስመጣት በቢሊዮን የሚቆጠር ብር ወጪ ተደርጓል። ባቡርስ? የባቡር ነገርማ ከሌሎችም የባሰ ሆኗል። የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ እንደተጠቀሰው ቢሆን ኖሮ፤ አገሪቱ ዘንድሮ 1700 ኪሎሜትር የባቡር ሃዲድና የባቡር ትራንስፖርት ይኖራት ነበር። ቢያንስ ቢያንስ የጂቡቲ መስመር ተሰርቶ አገልግሎት መስጠት ይጀምር ነበር። ግን እንደ እቅዱ አልሆነም። እስካሁን የተሰራው ሃዲድ “የ650 ኪሎሜትር 15%” ነው ተብሏል።

ቢበዛ ከመቶ ኪሎሜትር አይበልጥም ማለት ነው። የጂቡቲ መስመር ሁለተኛው ደግሞ ገና የአፈር ቁፋሮ ላይ ነው። ወደ ሰሜን ወደ ምዕራብ አቅጣጫ የተባሉት የባቡር መስመሮችማ ገና ዲዛይናቸው አላለቀም። የኮንዶሚኒዬም ቤት ግንባታም ተመሳሳይ ነው። ስለ ኮንዶሚኒዬም ብዙ ብዙ እቅዶች ሲዘረዘሩና በሪፖርት ሲቀርቡ አይገርማችሁም? በየአመቱ 50ሺ ኮንዶሚኒዬም ቤቶች ይገነባሉ ሲባል ትዝ ይላችኋል - በ97 ዓም። አንድ ሶስተኛውን እንኳ ማሟላት አልተቻለም። በእድገትና ትራንስፎርሜሽ እቅድ ላይ፣ አመታዊው የግንባታ መጠን ወደ 30ሺ ዝቅ እንዲል ተደረገ - በሶስት አመት 90ሺ መሆኑ ነው። ይሄም አልተቻለም። በሶስት አመት ውስጥ ለነዋሪዎች የደረሱ አዳዲስ የቤት ግንባታዎች ሲቆጠሩ፣ በአመት ከአስር ሺ አይበልጡም - የእቅዱ 30 በመቶ እንደማለት ነው። ጠቅላላ የኢኮኖሚውን አዝማሚያ በግልፅ የሚያሳይ ሌላ መረጃ ከፈለጋችሁ፤ በኤክስፖርት የሚገኘውን ገቢ መመልከት ትችላላችሁ። የእድገትና የትራንፎርሜሽን እቅድ የተዘጋጀው፤ በ2002 ዓ.ም ከሸቀጦች ኤክስፖርት 2 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ከተገኘ በኋላ ነው።

አምስት አመት ውስጥ በአራት እጥፍ አድጎ 8 ቢሊዮን ዶላር እንዲደርስ ታስቦ በወጣው እቅድ መሰረት፣ ዘንድሮ ወደ 5 ቢሊዮን ዶላር ገደማ የኤክስፖርት ገቢ መገኘት ነበረበት። ግን ሊሆን አይችልም። ለዚህም ነው እቅዱ ተከልሶ፣ በዚህ አመት ከኤክስፖርት 3.7 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት የታቀደው። ይሄም አልተሳካም። በስምንት ወራት ውስጥ የተገኘው የኤክስፖርት ገቢ 2 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነው። በአመቱ መጨረሻ ቢበዛ ቢበዛ 3 ቢሊዮን ዶላር ሊደርስ ይችላል። የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ ፈፅሞ ሊሳካ እንደማይችል ሁነኛ ማረጋገጫ የሚሆንብን፣ ይሄው የኤክስፖርት ገቢ ዝቅተኛነት ነው። ለምን ቢሉ፤ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ አገኛለሁ በሚል ሃሳብ መንግስት ያቀዳቸው በርካታ ፕሮጀክቶች ተግባራዊ ሊሆኑ አይችሉም። በትምህርትና በስልጠና በኩልስ፣ እቅዱ እየተሳካ ነው? ቃላትን ማንበብ የማይችሉ ተማሪዎች ምን ያህል ብዙ እንደሆኑ የተለያዩ ጥናቶችን በማጣቀስ መልስ መስጠት ይቻላል። ግን፣ በኢትዮጵያ ሬድዮ የተሰራጨ አንድ ዜና ብቻ በመስማት የአገሪቱን የትምህርት ሁኔታ አዝማሚያውን መገመት የሚቻል ይመስለኛል።

የቴክኒክ ኮሌጅ ውስጥ ከወዳደቁ እቃዎች መበየጃ ተሰራ የሚል ነው የዜናው ርዕስ። በኢትዮጵያ ሬድዮ የምንሰማቸው ዜናዎች “አስገራሚ” አይደሉ? ረቡዕ ማታ ሁለት ሰዓት ላይ፣ የእለቱ ሁለተኛ ትልቅ ዜና፣ በጅጅጋ የቴክኒክ ኮሌጅ፣ ከወዳደቁ ነገሮች መበየጃ እንደተሰራ ይገልፃል። በየጉራንጉሩ የሚዘጋጀውን መበየጃ፣ ለአንድ የቴክኒክ ኮሌጅ እንደ ትልቅ ስራ መቆጠር የጀመረው ከመቼ ወዲህ ይሆን? ግርድፍ “ትራንስፎርመር” እንደማለትኮ ነው። ከመበየጃ ጋር ሲነፃፀር፣ የሞባይል ቻርጀር እጅግ የተራቀቀ “ትራንስፎርመር” ነው። የኮሌጁ አስተማሪዎችና ተማሪዎች፣ መበየጃ ለመስራት መጣራቸው ስህተት ባይሆንም፣ መበየጃው “ከወዳደቁ ነገሮች” የተሰራው ኮሌጁ ምን አይነት ቢሆን ነው? መበየጃ ለመስራት የሚያስችል ቁሳቁስ ከሌለው፣ እንደ ሞተርና ጄነሬተር የመሳሰሉ ነገሮችን ለማደስማ ጨርሶ አይታሰብም ማለት ነው። የቴክኒክ ኮሌጅ እንዲህ ነው? ካስታወሳችሁ፣ የረቡዕ ማታ የመጀመሪያ ዜና፣ ጠ/ሚ ኃይለማርያም ለፓርላማ ያቀረቡትን ሪፖርት የሚመለከት ነበር። ለኢንዱስትሪ ምርትና ልማት ከፍተኛ ትኩረት እንደተሰጠው የገለፁት ጠ/ሚ ኃይለማርያም፣ ለቴክኒክ ትምህርት ስለሚመደበው በጀትና ስለ ትምህርት ጥራት ልብን የሚያሞቅ ሪፖርት ዘርዝረዋል። ታዲያ ይህንን “የምስራች” የሚያፈርስ “የመበየጃ” ዜና ወዲያውኑ ተከትሎ መቅረቡ አይገርምም?

“ከዳያስፖራ ደጋፊዎች የምናገኘው ምላሽ አበረታች ነው”

በአንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ (አንድነት) የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢና በመድረክ የብሔራዊ ምክር ቤት አባል የሆኑት አቶ ተመስገን ዘውዴ፤ በሁለቱ ድርጅቶች ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ለመምከርና በዲፕሎማሲና በፋይናንስ ድጋፍ ዙሪያ ከውጭ ደጋፊዎቻቸው ጋር ለመወያየት ትላንትና ወደ አሜሪካ ተጓዙ፡፡ በአንድነት እቅድና ስትራቴጂ መሠረት የውጭ ጉዳይ ቋሚ ኮሚቴው በጊዜው ከኢትዮጵያ ውጭ ያሉ ኢትዮጵያዊያን ደጋፊዎች በዲፕሎማሲ እና በፋይናንስ ፓርቲውን የሚረዱበትን ሁኔታ ማፈላለግና በሀገራቸው ጉዳይ እንዲደራጁ የማድረግ ሃላፊነት እንዳለበት የገለፁት አቶ ተመስገን፤ ጥረቱ በፊት የተጀመረ እንደሆነና ይህንኑ ጥረት አጠናክሮ ለመቀጠል ወደ አሜሪካ መጓዛቸውን ተናግረዋል፡፡

“ከዚህ በፊት እንደተለመደው በሀገሪቱ ወቅታዊ ጉዳይ፣ ስለ አደረጃጀትና የፋይናንስ ድጋፍ ለደጋፊዎች ገለፃ አደርጋለሁ” ያሉት አቶ ተመስገን፤ ጉዟቸው ዋሽንግተን ዲሲ፣ ካናዳና ደቡብ አፍሪካን እንደሚሸፍን ገልፀዋል፡፡ ቀደም ባለው ጊዜ በአሜሪካ 10 ያህል ግዛቶች ተዘዋውረው አባላትን አደራጅተው መመለሳቸውን ገልፀው፤ በአሁኑ ጉዞ በአሜሪካ ውስጥ የሚዘዋወሩባቸው ስቴቶች አሜሪካ በሚገኙ የድርጅት ሃላፊዎች ፕሮግራም እንደሚወሰን ተናግረዋል፡፡ ድጋፍ በማሰባሰብ፣ በአደረጃጀት፣ በዲፕሎማሲና በፋይናንስ ድጋፍ ለሚሠሩት ሥራ አምስት ወራትን በአሜሪካ በካናዳና ደቡብ አፍሪካ እንደሚቆዩና ነሐሴ መጨረሻ አሊያም መስከረም መጀመሪያ ላይ ወደ ሀገራቸው እንደሚመለሱ አቶ ተመስገን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

የአንድነትና የመድረክ ደጋፊዎች በተለይ በዋሽንግተን ዲሲ ሲያትል፣ በካሊፎርኒያ ቦስተን፣ አትላንታ፣ በዴንቨርና በሌሎች በርካታ ግዛቶች እንደሚገኙ ገልፀው የድርጅቱ ሃላፊዎች ባላቸው ፕሮግራም ቢቻል ሁሉንም አዳርሰው፣ አደረጃጀቱንና የፋይናንስ ድጋፉን ለማጠናከር እንደሚጥሩ ተናግረዋል፡፡ የኢትዮጵያ የተቃውሞ ፖለቲካ በመቀዛቀዙ የዲያስፖራውም ድጋፍ ተቀዛቅዟል በሚባልበት በአሁኑ ወቅት ከውጭው ደጋፊ ምን ይጠብቃሉ ተብለው ለተጠየቁት ሲመልሱ “ኢትዮጵያዊያን ደጋፊዎቻችንና ወገኖቻችን በምንም ሁኔታ ውስጥ ሆነው ስለገራቸው ያላቸው ስሜት ከፍተኛ ነው” ያሉት አቶ ተመስገን፤ አንድነትም ሲያደራጃቸው በህጋዊና በሠላማዊ መንገድ በመሆኑ ህጋዊ የዴሞክራሲ ሽግግር እንዲኖር የሚፈልጉ ኢትዮጵያዊያን በምንም ሁኔታ ከመደራጀትና ከመደገፍ ወደኋላ እንዳላሉ፣ ተቀዛቅዟል የሚባለውም ሀሰት እንደሆነ ተናግረዋል።

“እነዚህ በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ህጋዊ የስልጣንና የዴሞክራሲ ሽግግር እንዲኖር ፍላጐት ያላቸው ስለመሆኑ በደንብ እናውቃለን” ብለዋል። የሀገራቸው የልማትና የደህንነት ጉዳይ፣ የሰብአዊ መብት መከበር፣ የህዝብ የስልጣን ባለቤትነት የሚያገባቸው በመሆኑ የሀገር ውስጥ ሠላማዊ ትግልን ከመደገፍ፣ ከመደራጀትና በሠላማዊ መንገድ ከመታገል ቦዝነው እንደማያውቁ በአጽንኦት የገለፁት ሃላፊው፤ በአንድነትና በመድረክ ደጋፊዎች መካከል አንዳችም መቀዛቀዝ እንዳልታየ ተናግረዋል፡፡

“ይህን ጉዳይ ከዚህ ቀደም ወደ እነርሱ እየሄድን ስናደራጅና ስንቀሰቅስ አይተነዋል” ያሉት አቶ ተመስገን፤ ዛሬም እንደተለመደው ሠላማዊና ህጋዊ ትግሉን አጠናክሮ በመቀጠል የኢትዮጵያ ህዝብ የስልጣን ባለቤት እንዲሆን፣ ሰብአዊ መብቱ እንዲጠበቅ፣ የመድብለ ፓርቲ ስርዓትና ዴሞክራሲ በዚህች አገር እውን እንዲሆን መታገል እንዳለባቸው እንደሚያስረዱ ገልፀዋል፡፡ በዚህም እንደ በፊቱ ሁሉ ስኬታማና የተዋጣለት የማደራጀትና የድጋፍ ማሰባሰብ ስራ ሰርተው እንደሚመለሱ እምነታቸውን ገልፀዋል፡፡ “እንኳን እዚያ ሄደን አገር ውስጥም ሆነን ከዳያስፖራ ደጋፊዎች የምናገኘው ምላሽ አበረታች ነው” ብለዋል - አቶ ተመስገን፡፡