Administrator

Administrator


        “የአለማችን ቁጥር አንድ ፉንጋ ተብዬ፣ የአገሬን ስም አስጠራለሁ!” ብሏል

   ባለማማር ውስጥ ያለውን ውበት የማሳየት ዓላማ ይዞ በዚምባቡዌ በየአመቱ በሚካሄደው የ“አቶ መልከ-ጥፉ - ዚምባቡዌ” የቁንጅና ውድድር ለሁለት ጊዜያት አሸናፊ የነበረው ሚሊያም ማስቪኑ የተባለው የአገሪቱ ዜጋ፤ዘንድሮም ክብሩን በማስጠበቅ ሃትሪክ መስራቱንና የፉንጋነቱን ዘውድ መድፋቱን ኦል አፍሪካ ዶት ኮም ዘግቧል፡፡
በመዲናዋ ሃራሬ ባለፈው እሁድ ምሽት ለአምስተኛ ጊዜ በተከናወነው የ2017 “አቶ መልከ-ጥፉ” የቁንጅና ውድድር ላይ በዕጩነት ከቀረቡ አራት ተወዳዳሪዎች መካከል አንደኛ በመውጣት ብሄራዊውን የፉንጋነት ዘውድ የደፋው ማስቪኑ፤ ከውድድሩ አዘጋጅ ድርጅት የ500 ዶላር እና የአንዲት ላም ሽልማት ተበርክቶለታል፡፡
“በመላው ዚምባቡዌ ከእኔ ጋር የሚስተካከል አስጠሊታ ሰው እንደሌለ ሳይታለም የተፈታ ነው!... በቀጣይ ይህንን ፉንጋ መልኬን ይዤ አገሬን በአለም መድረክ ላይ በኩራት ለማቆምና ስሟን ለማስጠራት የቻልኩትን ሁሉ አደርጋለሁ፡፡ እርግጠኛ ነኝ፤ የ2018 የአለማችን ፉንጋ ክብርን በመጎናጸፍ፣ የአገሬን ስም በአለም አደባባይ አስጠራለሁ!” ብሏል ማስቪኑ፤ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ባደረገው ንግግር፡፡
የ2018 የአለማችን “አቶ መልከ-ጥፉ” የቁንጅና ውድድር በደቡብ አፍሪካ እንደሚካሄድ የጠቆመው ዘገባው፤ በብሄራዊ ደረጃ አሸናፊ የሆኑ የተለያዩ አገራት መልከ-ጥፉዎች፣ አገራቸውን ወክለው እንደሚወዳደሩና ከፍተኛ ፉክክር ይታይበታል ተብሎ እንደሚጠበቅም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

ትውልደ ኢትዮጵያዊው አቤል ተስፋዬ፤ በ92 ሚ. ዶላር 4ኛ ደረጃን ይዟል

    በአለማችን የሙዚቃ ኢንዱስትሪ ከፍተኛ አመታዊ ገቢ ያገኙ ድምጻውያንን ደረጃ የሚያወጣው ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት፣ ከሰሞኑም የ2017 የፈረንጆች አመት ከፍተኛ ተከፋይ የአለማችን ድምጻውያንን ዝርዝር ይፋ ያደረገ ሲሆን ፒዲዲ በ130 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በአንደኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
ፒዲዲ ባለፉት 12 ወራት ብቻ በድምሩ 130 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን የጠቆመው ፎርብስ፤ ከፍተኛ ገቢ ካስገኙለት መካከልም ሲሮክ ቮድካ ከተባለው ኩባንያ ጋር የገባው የንግድ ስምምነት፣ የኩባንያዎቹን ከፊል ድርሻ መሸጡና ባድቦይ ሪዩኒየን በሚል ርዕስ ያደረገው የሙዚቃ ኮንሰርት ጉዞው እንደሚጠቀሱ ገልጧል፡፡
አሜሪካዊቷ ድምጻዊት ቢዮንሴ ኖውልስ 105 ሚሊዮን ዶላር በማግኘት በአመቱ ሁለተኛውን ከፍተኛ ገቢ ያገኘች የአለማችን ድምጻዊት ስትባል፣ ድሬክ በ94 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
በቅጽል ስሙ ዘ ዊክንድ ተብሎ የሚጠራው ትውልደ ኢትዮጵያዊው የግራሚ ተሸላሚ አቤል ተስፋዬ፣ በ92 ሚሊዮን ዶላር አራተኛ ደረጃን መያዙን የጠቆመው የፎርብስ መግለጫ፤ የእንግሊዙ የሙዚቃ ቡድን ኮልድፕሌይ በበኩሉ፣ በ88 ሚሊዮን ዶላር አመታዊ ገቢ አምስተኛ ደረጃን መያዙን አመልክቷል፡፡
83.5 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት በደረጃ ሰንጠረዡ ሰባተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠው የ23 አመቱ ራፐር ጀስቲን ቢበር፤ ከአመቱ የፎርብስ የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ ድምጻውያን መካከል በእድሜ ትንሹ ነው ተብሏል፡፡

በህገወጥ መንገድ በሚመረቱ፣ ጥራት በሌላቸውና ኦሪጅናል ባልሆኑ የአይፎን ቻርጀሮችና በሌሎች ቻርጀሮች የአይፎን የሞባይል ስልኮችን ቻርጅ ማድረግ የእሳት አደጋን፣ በኤሌክትሪክ የመያዝና ከፍተኛ የመቁሰል አደጋን የማስከተል እድላቸው እጅግ ከፍተኛ መሆኑን ዘ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡
መሰል ቻርጀሮች ምንም እንኳን በአነስተኛ ዋጋ ቢገዙም ለአደጋ የማጋለጥ እድላቸው እጅግ ከፍተኛ መሆኑን በእንግሊዝ አገር በሰራሁት የደህንነት ፍተሻ ጥናት ደርሼበታለሁ ያለው ኤሌክትሪካል ሴፍቲ ፈርስት የተባለ የአገሪቱ ተቋም፤ ጥናት ካደረግኩባቸው ቻርጀሮች መካከል 98 በመቶው እጅግ አደገኛ እንደሆኑ አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡
ጥናት ከተደረገባቸው አይፎንን ቻርጅ ማድረግ የሚችሉ ሌሎች 50 አይነት ቻርጀሮች ውስጥ ከአንዱ በስተቀር ሌሎቹ የተለያዩ አይነት የደህንነት መስፈርቶችን ያላሟሉ ሆነው መገኘታቸውንም ተቋሙ አስታውቋል፡፡ አይፎንን ቻርጅ በሚያደርጉ ሌሎች 400 አይነት ቻርጀሮች ላይ በአሜሪካ ባለፈው አመት በተሰራ ሌላ ተመሳሳይ ጥናት፣ ቻርጀሮቹ የመበላሸትና አደጋ የማስከተል እድላቸው 99 በመቶ ያህል መሆኑ መረጋገጡንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

 ለአመታት ተባብሶ በቀጠለው የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ፣ እየተገባደደ ባለው የፈረንጆች አመት 2017 ብቻ 1.7 ሚሊዮን ያህል የአገሪቱ ዜጎች፣ከመኖሪያ ቦታቸው መፈናቀላቸውንና ወደ ሌሎች አገራት መሰደዳቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በአገሪቱ ለአመታት የዘለቀው የእርስ በእርስ ግጭትና ጦርነት ዜጎችን ለከፋ የሰብዓዊ ቀውስ መዳረጉን ቀጥሏል ያለው ዘገባው፤ ባለፈው አመት መከናወን የነበረበት ምርጫ በታቀደለት ጊዜ አለመካሄዱ የእርስ በእርስ ግጭቱን ወደከፋ ሁኔታ እንዳሸጋገረውና ግጭቱን በመሸሽ ከመኖሪያ ቦታቸው የሚፈናቀሉና ወደተለያዩ አገራት የሚሰደዱ ዜጎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን አመልክቷል፡፡ ኢንተርናል ዲስፕለስመንት ሞኒተሪንግ ሴንተር የተባለው ተቋም ባወጣው አዲስ ሪፖርት፤ በዘንድሮው አመት ብቻ በየዕለቱ በአማካይ 5 ሺህ 500 የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ዜጎች ከመኖሪያ ቤታቸው መፈናቀላቸውን አስታውቋል ያለው ዘገባው፤ የመፈናቀሉ መጠን በአለማቀፍ ደረጃ የከፋውና ብዙዎችን ተጠቂ ያደረገ ነው ማለቱን ገልጧል፡፡
በአገሪቱ ከመኖሪያ ቦታቸው የተፈናቀሉ ዜጎች ቁጥር በድምሩ አራት ሚሊዮን ያህል መድረሱንና ከሰባት ሚሊዮን በላይ ዜጎችም የምግብ እጥረት ተጎጂ መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ሰብዓዊ ቀውሱን ለመግታት የሚደረገው አለማቀፍ ድጋፍ ግን እጅግ አናሳ ነው መባሉን አመልክቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ካሳኢ በተባለው የአገሪቱ አካባቢ ተባብሶ በቀጠለው የእርስ በእርስ ግጭት ሳቢያ ግማሽ ሚሊዮን ያህል የአገሪቱ ዜጎች ለምግብ እጥረት መዳረጋቸውንና ተገቢ እርዳታ አለማግኘታቸውን የአለም የምግብ ፕሮግራም ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡

 የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባለፈው ረቡዕ “እየሩሳሌም የእስራኤል ዋና ከተማ መሆኗን እውቅና ሰጥቻለሁ፤ በእስራኤል የሚገኘውን የአሜሪካ ኤምባሲም ከቴል አቪቭ ወደ እየሩሳሌም አዘዋውራለሁ” ማለታቸውን ተከትሎ፣ መካከለኛው ምስራቅን ጨምሮ ከመላው አለም እጅግ ከፍተኛ ውግዘት እየገጠማቸው ይገኛል፡፡
የእየሩሳሌም ጉዳይ በሁለቱ ወገኖች መግባባትና ድርድር ይፈታ የሚለውንና አሜሪካ ለአስርት አመታት ስታራምደው የቆየቺውን አቋም፣ ጊዜው ያለፈበትና የማያዋጣ ብሎ በድንገት በናደውና አለምን ባነጋገረው የትራምፕ ንግግር ክፉኛ የተቆጡ ፍልስጤማውያን ተቃውሟቸውን ያሰሙ ሲሆን ጉዳዩን የሚያወግዙ መንግስታት ቁጥርም እያደገ ነው፡፡
የፍልስጤሙ ፕሬዚዳንት መሃሙድ አባስ፤”አሜሪካ ከአሁን በኋላ በእስራኤልና በፍልስጤም መካከል የአደራዳሪነትና የሸምጋይነት ቦታ የላትም” ያሉ ሲሆን፣ ይህ አደገኛ ውሳኔ በሁለቱ አገራት መካከል ያለውን የሰላም መንገድ እንዲሁም የአካባቢውን ብሎም የመላውን አለም ሰላምና መረጋጋት አደጋ ላይ የሚጥል ነው ሲሉ የትራምፕን ንግግር ነቅፈዋል፡፡
የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ናታኒያሁ በበኩላቸው፤ “ለዚህ ታሪካዊ ውሳኔዎት እጅግ አመሰግንዎታለሁ፤ አይሁዳውያንና የአይሁዳውያን አገር ሁሌም ሲያመሰግኑዎት ይኖራሉ” በማለት ትራምፕን ማመስገናቸውን ሲኤንቢሲ ዘግቧል፡፡
የሃማሱ መሪ ኢስማኤል ሃኒ በበኩላቸው፤ ከጋዛ ሰርጥ ባስተላለፈው መልዕክት፣ “ትራምፕ በፍልስጤማውያን ላይ ጦርነት አውጇልና፣ ሴት ወንድ ህጻን አዛውንት ሳትሉ ታጥቃችሁ ተነሱ፤ ከእስራኤል ጋር ለምንፋለምበት አዲሱ ኢንቲፋዳ ተዘጋጁ” ሲሉ ለፍልስጤማውያን በይፋ የክተት አዋጅ ጥሪውን አስተላልፈዋል፡፡ ይህን ተከትሎም፣ በርካታ ፍልስጤማውያን ከትናንት በስቲያ መደበኛ እንቅስቃሴያቸውን አቋርጠው፣ ወደ ጋዛ ጎዳናዎች በመጉረፍ፣ በቁጣ እየነደዱ የትራምፕን ፎቶግራፍና የአሜሪካን ባንዲራ አቃጥለዋል፡፡
“ሰውዬው መካከለኛው ምስራቅ ላይ የማይጠፋ እሳት ለኮሰ!” ሲሉ የትራምፕን ንግግር አደገኛነት የገለጹት የቱርኩ ፕሬዚዳንት ጠይብ ኤርዶጋን ሲሆኑ፣ የግብጹ አቻቸው አብዱል ፋታህ አልሲሲ በበኩላቸው፤ የትራምፕ አካሄድ የሰላም ዕድሎችን የሚዘጋ ነው ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
ኢራን፣ ሊባኖስና ኳታር የትራምፕን ውሳኔ በአደባባይ የነቀፉ ሲሆን ወገንተኝነቷ ለአሜሪካ ነው የምትባለው ሳዑዲ አረቢያ ሳትቀር፣ የትራምፕን ውሳኔ ተገቢነት የሌለውና ሃላፊነት ከማይሰማው ሰው የሚጠበቅ ስትል ነቅፋዋለች፡፡ የአሜሪካ ወዳጅ የምትባለው ዮርዳኖስም በተመሳሳይ ሁኔታ የትራምፕን ንግግር በአደባባይ አውግዛለች፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትራምፕ ውሳኔ ለእስራኤላውያንና ለፍልስጤማውያን የማይበጅ፣ የሰላም ጥረትን የሚያጨናግፍ አደገኛ አካሄድ ነው ማለታቸውን የዘገበው ቢቢሲ፤ እንግሊዝ፣ ጣሊያንና ፈረንሳይን ጨምሮ ስምንት የተመድ የጸጥታው ምክር ቤት አባል አገራት ያቀረቡትን ጥያቄ መሰረት በማድረግ፣ ምክር ቤቱ በጉዳዩ ዙሪያ ለመምከር ትናንት ቀጠሮ መያዙንም አመልክቷል፡፡
የአውሮፓ ህብረት ትርጉም ያለው የሰላም ሂደት እንደገና እንዲቀጥል ጥሪ ያቀረበ ሲሆን የእንግሊዝ መንግስት የትራምፕን ውሳኔ “የማያተርፍ” ሲል በይፋ ነቅፎታል፤ ስዊድን፣ ፈረንሳይና ጀርመንም “ጉዳዩ በሁለቱ አገራት የጋራ ስምምነት እልባት ማግኘት ሲገባው ትራምፕ ጣልቃ ገብተው አደገኛ ነገር መናገራቸውን አልወደድነውም” የሚል ተመሳሳይ አቋም አንጸባርቀዋል፡፡
አለም በአንድ ድምጽ ውግዘቱን የሚያወርድባቸው ትራምፕ ግን፣ “ጉዳዩ የምታጋንኑትን ያህል አይደለም፤ ለእውነታ እውቅና መስጠት ነው” ሲሉ ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡
በመካከለኛው ምስራቅ እና በአንዳንድ የአፍሪካ አገራት የሚገኙ የአሜሪካ ኢምባሲዎች በበኩላቸው፤ ሊቀሰቀሱ ከሚችሉ ተቃውሞዎች፣ አመጾችና ብጥብጦች ራሳችሁን ጠብቁ ሲሉ ዜጎቻቸውን አስጠንቅቀዋል፡፡
አደገኛ ጥፋትን የሚያስከትል አጉል ውሳኔ ሲል የትራምፕን አካሄድ ያወገዘው የአረብ ሊግ አባል አገራት፤ ዛሬ በቱርክ ተሰብስበው በጉዳዩ ዙሪያ ለመምከር ቀጠሮ መያዛቸውንም ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

ተወልደው ያደጉት በባህርዳር ዙሪያ ጣና አካባቢ ነው፡፡ ቤተሰቦቻቸው ዓሳ አስጋሪዎች ነበሩ፡፡ ከልጅነታቸው አንስተው ዓሳ እያሰገሩ ነው ያደጉት፡፡ የዓሳ ኮርፖሬሽን የሚባለው የመንግስት ድርጅት ተቋቁሞ፣በግል ዓሳ ማስገር ሲከለከል የሥራ ዘርፋቸውን ቀየሩ፡፡ የተለያዩ ሸቀጣ ሸቀጦችን እየገዙ በበቅሎ መሸጥ እንደጀመሩ ይናገራሉ - የዛሬው ኢንቨስተር አቶ ካሣሁን ምስጋናው፡፡ በ1982 ዓ.ም በራሳቸው ስም ንግድ የጀመሩት ባለሃብቱ፤ከመንግስት ለውጥ በኋላ በፀደቀው የንግድ ህግ መሰረት ድርጅታቸውን ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ ፒኤልሲ ብለው በማቋቋም በከፊል ተቋራጭነትና በማሽነሪ ኪራይ ሥራ የጀመሩ ሲሆን ዛሬ የ5 ቢሊዮን ብር ኢንቨስትመንት ባለቤትና የ5 ሺህ ሰራተኞች ቀጣሪ ለመሆን በቅተዋል፡፡
         ባለሀብቱ በቅርቡ በባህርዳር 360 ሚ. ብር የፈጁ የእብነበረድና የቀለም ፋብሪካዎችን ገንብተው አስመርቀዋል፡፡ በቅርቡ ሥራ የሚጀምር የዘይት ፋብሪካም እየተከሉ ነው፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ ባለሀብቱ ከዓሳ ማስገር ተነስተው አሁን እስከደረሱበት ስኬት ያለውን ጉዞ ከባለሃብቱ ጋር ባደረገችው ቃለ ምልልስ ታስቃኘናለች፡፡ የወደፊት ዕቅዳቸውንና ህልማቸውንም አውግተዋታል፡፡ የአቶ ካሣሁን ምስጋናውን አስደማሚ የንግድ ሥራ ግስጋሴ ከአንደበታቸው እነሆ፡-


    ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ እንዴት ነው የተመሰረተው?
ስለ ቢአኤካ ከመናገሬ በፊት በግል ስሜ ነበር የንግድ ስራዬን የጀመርኩት፡፡ እስከ 1982 ዓ.ም በግል ስሜ ስሰራ ከቆየሁ በኋላ በአገራችን በተፈጠረው የኢኮኖሚ እንቅስቃሴና ለውጥ ፒኤልሲ የሚባል ነገር ሲመጣ፣ ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ በሚል አቋቁመን መስራት ጀመርን ማለት ነው፡፡ ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ  ቀደም ብለው የነበሩትን የእኔን ልምዶችና ሀብት ይዞ ነው የተመሰረተው፡፡
ቢአኤካ ሲመሰረት መጀመሪያ ምን ነበር የሚሰራው?
መጀመሪያ የተነሳነው በኮንስትራክሽን ሥራ ነበር፡፡ ስራ የጀመርነው ከፊል ተቋራጭ በመሆንና የኮንስትራክሽን ማሽነሪዎች በማከራየት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ደግሞ ወደ ግብርና ገባን፡፡ ግብርናው በቡና እርሻ ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ዛሬ ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ፣ 2700 ሄክታር መሬት ላይ ቡና ያለማል፡፡ ሰፊ የቡና እርሻ ያለው ድርጅት ነው፡፡
በአስመጪና ላኪነት ላይም መሰማራታችሁን ሰምቻለሁ---
እውነት ነው፡፡ እንግዲህ ሰፊ የቡና እርሻ ባለቤት እንደመሆናችን፣ ቡና በአብዛኛው ወደ ውጭ የሚላክ በመሆኑ የራሳችንን ቡና በጥራት እሴት ጨምረን ለመላክ በኤክስፖርቱ ዘርፍ ተሰማራን፡፡ ቡናው ለመላክ እስኪደርስ በሰሊጥና በአጠቃላይ በጥራጥሬና በቅባት እህሎች የላኪነት ስራውን ስንሰራ ቆየን፡፡ ድርጅታችን በቅባት እህሎችና ጥራጥሬ ይዞት የቆየውን ልምድ በመንተራስ፣ ከራሱ እርሻ “ስፔሻሊቲ ቡና” የሚባል የቡና ምርት ለውጭ ገበያ መላክ ጀመረ፡፡
የቡና እርሻችሁ የት ነው የሚገኘው?
የቡና እርሻው በማጂንግ ዞን ጎደሬ የተባለ ወረዳ ውስጥ ይገኛል፤
የምትልኩት “ስፔሻሊቲ ቡና” ከሌላው የቡና ምርት ልዩነቱ ምንድን ነው?
ቡናው በጣም ኦርጋኒክ ነው፤ ከየትኛውም ንክኪ ነፃ የሆነና ደረጃውን የጠበቀ ቡና ሲሆን ለዚህም የተሰጠን ሰርተፍኬት አለ፡፡ አሁን በቅርቡ መንግስት ባሻሻለው የቡናና ሻይ አዋጅ፤ “አውት ግሮስ” የተባለ የአካባቢውን ቡና እርሻ ያላቸው ኢንቨስተሮች፣ ጥራቱን በጠበቀ መልኩ ይላኩ በሚለው መሰረት፤ እኛም የአካባቢውን ቡና እየገዛን፣ ከራሳችን ቡና ጋር እያደረግን ደረጃውን የጠበቀ “ስፔሻሊቲ ቡና” በተለይም ለአውሮፓ ገበያ እንልካለን፡፡ ድርጅታችን ኤክስፖርቱን በማስፋፋት ለውጭ ገበያ የሚቀርቡ ምርቶችን ወደ ማምረት የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪ ገብቷል፡፡ በቅርቡ ሥራ የጀመረው “ኮከብ የእብነበረድ ፋብሪካ” ለዚህ ተጠቃሽ ነው፡፡ ፋብሪካው ለጊዜው የእብነበረድ ምርቱን ለአገር ውስጥ ገበያ ያቅርብ እንጂ በሁለት መልኩ ለውጭ ገበያ ያቀርባል፡፡
በሁለት አይነት ሲባል ምን ማለት ነው?
አንደኛው ቀጥታ ከቦታው የእብነብረድ ቋጥኝ ቆርጦ እንዳለ መላክ ነው፡፡ ሁለተኛው በደንብ ሰርቶና እሴት ጨምሮ ያለቀለት ምርት መላክ ነው። እንግዲህ ይህ ፋብሪካ ከ”ኮከብ ቀለም ፋብሪካ” ጋር በአንድ ላይ በ18ሺህ ካሬ ሜትር ላይ አርፎ፣ በባህርዳር ተገንብቷል፡፡ የእብነበረድና የቀለሙ ፋብሪካ በአጠቃላይ 360 ሚ. ብር ነው የወጣበት። የቀለም ፋብሪካው የተቋቋመበት ዋና አላማ የእብነበረዱን ተረፈ ምርት እየተጠቀመ፣ ጥራት ያለው የኳርትዝና የውሃ ቀለም ለማምረት ታስቦ ነው፡፡ ስለዚህ በተረፈ ምርትነት የሚጣል ነገር አይኖረውም፡፡ ፋብሪካዎቹ በሙሉ ሀይላቸው ስራ ሲጀምሩ ለ500 ሰዎች የስራ እድል ይፈጥራሉ። ሌላው እንግዲህ ምርቱ ወደ ውጭ ገበያ ሲቀርብ ትልቅ የውጭ ምንዛሪን ያመጣል፡፡ ጥቅማቸው ዘርፈ ብዙ ነው፡፡
የእብነበረዱ ጥሬ እቃ ምንጩ ከየት ነው?
ማዕድኑ የሚወጣው ማንኩሽ ከተባለ ቦታ ነው፡፡ እዛው ቦታ ላይ “ዳይመንድ ዋየር” የተባለ የእብነበረድ ፕሮስስ ማድረጊያ ፋብሪካም ተክለናል። ይህ ፋብሪካ የእብነበረዱ ማዕድን እንደወጣ እዛው እየቆረጠና እያስተካከለ ኤክስፖርት ለማድረግ ያግዛል፡፡ የቀለም ፋብሪካውንም ብንወስድ በዓመት 25 ሚ. ሊትር በላይ የማምረት አቅም ያለው ነው፡፡ ከአገር ውስጥ ገበያ ተርፎ ለጎረቤት አገራት ምርቱን ኤክስፖርት የማድረግ እቅድ ይዞ ነው እንቅስቃሴውን የጀመረው፡፡ ለዚህም ነው ከአገራችን አቅም በላይ የሆኑ የአውሮፓ ማሽኖችን መርጠን አምጥተን የተከልነው፡፡ ማሽኖቹ የጣሊያን የዴንማርክና የቤልጂየም ስሪት ናቸው፡፡ እነዚህ ማሽነሪዎች ኤክስፖርት የሚደረጉ ምርቶችን ለማምረት የሚረዱ ናቸው፡፡ በአሁኑ ሰዓት ሁለት ፋብሪካዎች በከፊል ስራ ጀምረዋል፡፡ እስካሁን በአንድ ሺፍት ነው የሚሰሩት፤ከ200 በላይ ሰራተኞች ሥራ ላይ ተሰማርተዋል፡፡
ቢአኤካ ጀነራል ቢዝነስ በአሁኑ ወቅት ጠቅላላ ኢንቨስትመንቱ ምን ያህል ነው? በአጠቃላይ ምን ያህል ሰራተኞች አሉት?
የድርጅቱ ጠቅላላ ኢንቨስትመንት ወደ 5 ቢ. ብር ነው፤ በስሩ ከ5 ሺህ በላይ ሰራተኞችን ይዟል። እንግዲህ በቀጣይ የሚከፈቱ ፋብሪካዎች አሉ፡፡ ከ5ሺህ ሰራተኞች ውስጥ ግማሽ ያህሉ በእርሻውና በኮንስትራክሽኑ ዘርፍ ላይ እየሰሩ ይገኛል፡፡
የኮንስትራክሽኑ ዘርፍ ምን ምን ስራዎችን ያከናውናል?
ኮንስትራክሽኑ በአገራችን የሚሰሩ ትልልቅ መንገዶችን፣ የባቡር መንገዶችንና እንደ ሳሊኒ ባሉ ትልልቅ ዓለማቀፍ ኩባንያዎች የሚገነቡ ፓወር ሀውሶችን “Earth work” ወይም የአፈር ስራዎችን በከፊል ቢአኤካ ነው የሚሰራው፡፡
የእብነበረድ ፋብሪካው የማምረት አቅሙ ምን ያህል ነው?
በዓመት 500 ሺህ ሜትር ካሬ ያለቀለት እብነበረድ ያመርታል፡፡ ይሄ በዳይመንድ ዋየር እየተቆረጠ እንዲሁ የሚላከውን ያላለቀለት እብነበረድ አይመለከትም፡፡ በዚህም በዓመት እስከ 5 ሚ. ዶላር የውጭ ምንዛሬ ለማግኘት እንደ ጅምር እቅድ የያዝን ሲሆን በሙሉ ሀይላችን ወደ ስራ ስንገባና የውጭ ገበያን ስናስፋፋ ገቢውን ወደ 10 ሚሊዮን ዶላር ለማድረስ አቅደን እየሰራን ነው፡፡ ይሄ ለአገርም ኢኮኖሚ የሚያበረክተው አስተዋፅኦ ቀላል አይደለም፡፡
ቢአኤካ እያስገነባቸው ያሉና በቀጣይ የሚገነቡ ፋብሪካዎችም እንዳሉ ይነገራል፡፡ እስቲ ስለዚህ ጉዳይ ያብራሩልን?
እንግዲህ ድርጅታችን ትኩረቱን ወደ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ አድርጓል፡፡ በቅርቡ የሚጠናቀቅና በአዲስ አበባ ዙሪያ ታጠቅ ኢንዱስትሪ መንደር እየተገነባ ያለ ትልቅ የዘይት ፋብሪካ አለን፡፡ ፋብሪካው 200 ሚ. ብር ነው የወጣበት፡፡ ዋና መጭመቂያ ማሽኑ የመጣው ከአሜሪካ ሲሆን መፍጫው ከቻይና፣ ማጣሪያው ከህንድ ነው የመጣው፡፡ በአሁኑ ሰዓት የውጭ አገር ባለሙያዎች መጥተው፣ የማሽን ተከላ ስራ እያካሄዱ ሲሆን ከአንድ ወር በኋላ ወደ ስራ ይገባል፡፡ ፋብሪካው በዓመት 10 ሚሊዮን ሊትር የሱፍ የኑግ፣ የሰሊጥ፣ የአኩሪ አተርና የተልባ ዘይት የማምረት አቅም ያለው ነው፡፡ ከፋብሪካው ብዙ ጠቃሚ አላማዎች መካከል አንዱ ደህንነቱ የተጠበቀ ዘይት ለአገራችን ህዝብ ማቅረብ ነው፡፡ ሁለተኛ ከውጭ የምናስመጣውን የፓልም ዘይት በማስቀረት የውጭ ምንዛሪን ማዳን ነው፡፡ በሌላ በኩል ለ200 ሰዎችም የስራ እድል የሚፈጥር ነው። እኛ ሰሊጥ ኑግ፣ አኩሪ አተር፣ ተልባና ሱፍ ወደ ውጭ እየላክን የፓልም ዘይት እናስገባለን፡፡ ያለንን ምርት እዚሁ ጤናማ ዘይት ለምን አናመርትበትም በሚል ታስቦ ነው የተቋቋመው፡፡ ከስድስት ወር በኋላ ወደ ተከላ የሚመጡ ሌሎች ፋብሪካዎችም አሉን፡፡ እነዚህ ፋብሪካዎች የግራናይትና የቴራዞ ፋብሪካዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ሁለት ፋብሪካዎች ልክ እንደ እብነበረዱና እንደ ቀለሙ ፋብሪካ ተመጋጋቢ ናቸው፡፡ የግራናይት ፋብሪካ ተረፈ ምርት ለቴራዞ ፋብሪካው ዋና ግብአት የሚሆን ነው፡፡ የማርብልና ግራናይት ፍቅፋቂ በመፍጨትና መልሶ በመጋገር ደረጃውን የጠበቀ ቴራዞ መስራት ይቻላል፡፡ እነዚህ ፋብሪካዎች በባህርዳር ነው የሚገነቡት፡፡ የሁለት ዓመት ዕቅድ የተያዘላቸው የሴራሚክስና የጥቅል መስታወት ፋብሪካዎችም ጠቅላላ ንድፍና ስራ አልቆ ከሁለት ዓመት በኋላ እውን ይሆናሉ፡፡ መሬት ወስደን ጨርሰናል፡፡ የነዚህ ምርቶች 98 በመቶ ጥሬ እቃ ከአገር ውስጥ የሚገኝ ነው፡፡
ሌላው በአዲስ አበባ ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ በ50 ሺህ ካሬ ሜትር ላይ “ጀነራል ኬሚካል እና ፓኪንግ” የሚባል ፋብሪካን ግንባታ ላይ ነው ያለነው፡፡ በዚህ መልኩ የማኑፋክቸሪንግ ኢንዱስትሪውን በሰፊው እየተቀላቀልን እንገኛለን፡፡ ለዚህም ቀን ከሌሊት ያለ እረፍት ነው የምንሰራው።
በንግድ ሥራ ስኬታማ ለመሆን የረዳዎት ትምህርት ወይም ልምድ ካለ ቢነግሩኝ---
እንግዲህ ወደ ኋላ ልትመልሺኝ ነው፡፡ እኔ ባህር ዳር ዙሪያ ነው ጣና አካባቢ ተወልጄ ያደግሁት። ዓሳ በማስገር ህይወት የሚመራ ቤተሰብ ልጅ ነኝ። ዓሳ በማስገርም ላይ ነበርኩ፡፡ በ1982 ዓ.ም አካባቢ የለውጡ ሰሞን ዓሳ ኮርፖሬሽን የሚባል ተቋቋመና ዓሳው ሁሉ ለኮርፖሬሽኑ እንዲሆንና ግለሰቦች ዓሳ እንዳያሰግሩ ሲከለከል፣ ከ7ኛ ወደ 8ኛ ክፍል ባለፍኩበት ወቅት ነበር ትምህርቴን አቋርጨ ሸቀጣ ሸቀጥ እየገዛሁ በበቅሎ እየሸጥኩ ንግድ የተለማመድኩት፡፡ ከ1983 ዓ.ም ለውጡ ተደርጎ አገር ነፃ ሆነ ከተባለ በኋላ መጀመሪያ ላይ እንደነገርኩሽ፣ መጀመሪያ በግል ስሜ፣ ከዚያም ፒኤልሲ ከፍቼ ስሰራ ቆይቼ እዚህ ደርሻለሁ፡፡ ይሄው ነው፡፡
እንዲህ አይነት ሰፊ ኢንቨስትመንት ላይ ለመሰማራት ከንግድ ፈቃድ ጀምሮ መሬት እስከመረከብ ከፍተኛ ውጣ ውረድና ቢሮክራሲ እንደሚያጋጥማቸው ብዙ ባለሀብቶች ሲያማርሩ ይሰማል፡፡ እርስዎ በዚህ ረገድ የገጠመዎት ችግር አለ?
ብዙዎች ቦታ ይወስዱና ለረጅም ጊዜ አጥረው ያስቀምጣሉ፡፡ እኛ አካባቢ አጥሮ የሚያስቀምጠውንና ቶሎ ወደ ሥራ የሚገባውን ለመለየት ከሚወስደው ጊዜ በስተቀር ምንም ችግር የለም፡፡ እኔም እስከ ዛሬ እሰራለሁ ያልኩትን በወቅቱና በአግባቡ እየሰራሁ በማሳየት ነው እዚህ የደረስኩት፡፡ እንደውም የበለጠ ትብብርና ድጋፍ እንጂ ያጋጠመኝ ችግር የለም፡፡ በዚህ ላይ ደግሞ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በፋብሪካው ምርቃት ላይ ባደረጉት ንግግር፤ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል፡፡ በስራ ላይ አንዳንድ ችግሮች አይጠፉም ግን በትዕግስት ማለፍ ያስፈልጋል፡፡ ያው በፋብሪካዎቹ በርካታ ሰዎች በመቅጠር ከሴራሚክሱ በካሬ 10 ብር፣ ከቀለም ፋብሪካው ከሊትር 10 ሳንቲም በመቁረጥ እንቦጭን ለመዋጋት የሚደረገውን ትግል በማገዝ፣ ለአገራችንና ለወገናችን የበኩላችንን እያደረግን እንገኛለን፡፡

 በደራሲና ዳይሬክተር በሀይሉ ዋሴ (ዋጄ) ተፅፎ የተዘጋጀውና በእውነት መልቲ ሚዲያ ፕሮዳክሽን ተዘጋጅቶ፣ በኧርሊ ኤ. ኤም መልቲ ሚዲያ የቀረበው “በእናት መንገድ” የተሰኘ ፊልም ከነገ በስቲያ ሰኞ ከቀኑ 11፡30 ጀምሮ በብሄራዊ ቴአትር እንደሚመረቅ አስተባባሪው ኢጋ ሚዲያ ኮሚዩኒኬሽን አስታወቀ፡፡
የድራማ ዘውግ ያለውና 1፡35 ርዝመት ያለው ፊልሙ፣ ተሰርቶ ለመጠናቀቅ 1 ዓመት ጊዜ እንደፈጀ የተነገረ ሲሆን 850 ሺ ብር እንደወጣበትም ተገልጿል፡፡  በፊልሙ ላይ ደሞዝ ጎሽሜ፣ ሜላት ሰለሞን፣ መስፍን ሀይለየሱስ፣ ብርሀኔ ገብሩ፣ አሸናፊ ዋሴ፣ ለምለም አበራ፣ ሰለሞን ተስፋዬና ሌሎችም የተወኑበት ሲሆን በሜላት ሰለሞን ፕሮዱዩስ መደረጉ ታውቋል፡፡

የክስታኔ ጉራጌ ሕዝብ የልማት ማህበር ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ባህሎች አካዴሚ ጋር በትብብር ያዘጋጀው ክስታንኛ - አማርኛ - እንግሊዝኛ መዝገበ ቃላት ነገ እሁድ ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ እስከ 6፡30 ባለው ጊዜ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቴአትር በይፋ ይመረቃል፡፡
ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በሚገኙበት በዚህ ሥነስርዓት ላይ በመገኘት የመርሃ ግብሩ ተሳታፊ ይሆኑ  ዘንድ ማህበሩ በአክብሮት ተጋብዘዋል፡፡


        “--የዚህ ጦርነት “ባለሞያው” ናቸው ስንል፣ እንዲኹ ከሜዳው ተነስተን አይደለም፡፡ ጥላሁን ይጽፋሉ፤ ከጻፉም ሌላ ጉዳይ የላቸውም- ይኼው የኢትዮጵያና ጣሊያን ጦርነት ብቻ!---”

    ርእስ- የኢትዮጵያና የጣሊያን ሁለተኛው ጦርነት ታሪክ
ደራሲ- ጥላሁን ጣሰው
የህትመት ዘመን -  2009 ዓ.ም
ገጽ- 209
ዋጋ- ብር 82.00  ($25.00)
ዳሰሳ፡- ሰሎሞን አበበ ቸኮል
ስለ ኢትዮ-ጣሊያን ጦርነት የትኛውንም ዓይነት መጽሐፍ ያነበበም፣ የትኛውንም ያህል የተማረውና የተመራመረውም ቢኾን፣ ይህን የጥላሁን ጣሰውን መጽሐፍ ካላነበበ፣ የተሟላ ወይም የተፈፀመ ግንዛቤ ሊኖረው አይችልም፡፡ ሌላው ቢቀር፣ “የጦርነቱ ጠቅላይ አዛዥ” ስለነበሩት ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ከጦርነቱ ጋር ያላቸውን የታወቀ ስም ፈጽሞ የሚቀይረው ነው፡፡ ይህ የጥላሁን ጣሰው የጦርነቱ ታሪክ መጽሐፍ ዕድለ ቢሱን ንጉሠ ነገሥት፣ ታላላቅ ጦርነቶችን በሚገባ ከመሩ የጦር መሪዎች እንደ አንዱ ይቆጥራቸዋል፡፡ እስከ ማይጨው ውሎአቸው ድረስ፣ ከዚያም በስደት ላይ ሳሉም የጦር መሪም ነበሩ፡፡ እንዲያውም፣ ይህ “ኹለተኛው” የተባለው የኢትዮጵያ ጣሊያን ጦርነት ታሪክ ተከታይ ዒላማውም፣ ይኼው የንጉሠ ነገሥቱ የጦር ምሪት ታሪክ ነው ሊባል ይችላል፡፡
ወልወል ላይ በ1927፣ ኅዳር 27 ቀን ድንገት በፈጸመችው ድብደባ፣ ጣሊያን “በይፋ ሳታሳውቅ” የከፈተችው የዚህ ጦርነት “ዓዋቂ” ወይም “ተጠያቂ” (ኤክስፐርት) ሊባሉ የሚበቁት ጥላሁን ጣሰው፤ የጦርነቱን ሙሉ ታሪክ ከእነ ትንታኔው፣ በ11 ምዕራፎች፣ ከ200 እምብዛም በማይጨምሩ ገጾች ክሽን አድርገው አቅርበውታል፡፡ በ1975 ዓ.ም በኩራዝ አሳታሚ ድርጅት የታተመ፣ “አዳባይ” የተባለ በዚኹ ጦርነት ላይ የተደረገ ረዥም የውጊያ ታሪካዊ ልብ ወለድ ጽፈዋል፡፡ “ትራይንግ ታይምስ” እንደ ፈረንጆች አቆጣጠር በ1911፣ በሻማ ቡክስ የታተመላቸው፣ ሌላው “የኹለተኛው ኢታሎ- ኢትዮጵያን” ጦርነት ልብወለድ መጽሐፋቸው ነው፡፡ ከዚህ ጦርነት ማግስት የነበረችውን ኢትዮጵያ፣ የኒዮ ፋሽስቶች መነሳትና መውደቅ፣ አብዮታውያኑንና ደርጋዊውያኑን የተመለከተ ታሪክን “ፎር ላቭ፡ ሎያሊቲ ፍሪደም ኤንድ ዲግኒቲ” በሚል ርእስ የጻፉም ናቸው፡፡ ከዚህ አርበኝነት ቀጥሎ ስለነበረው የ50ዎቹና 60ዎቹ ኢትዮጵያ ኹኔታ “ፍትሕና ርትዕ” የተባለ ሥራ በአማዞን አሳትመዋል፡፡
ከእነዚህም በተጨማሪ፣ በተለይ በ”ሪፖርተር” ጋዜጣ በዚሁ ጦርነት ላይ የተለያዩ ጽሑፎችን በአማርኛና በእንግሊዝኛ አቅርበዋል፡፡ “ኢትዮጵያን ኬዝ ኦፍ ዎር ክራይምስ አጌይንስት ሙሶሊኒ፣ ባደግሊዮ፣ ግራዝያኒ” (ሪፖ፣ ሴፕቴ፣ 2012)፤  እና “ዲፋይኒንግ ካራክተርስቲክስ ኦፍ ዘ ሰከንድ ኢትዮ - ኢታሊያን ዎር” (አፕ. 28፣ 2012) በኹለቱም የቀረበ ጽሑፎቻቸው ናቸው፡፡
የዚህ ጦርነት “ባለሞያው” ናቸው ስንል፣ እንዲኹ ከሜዳው ተነስተን አይደለም፡፡ ጥላሁን ይጽፋሉ፤ ከጻፉም ሌላ ጉዳይ የላቸውም- ይኼው የኢትዮጵያና ጣሊያን ጦርነት ብቻ! ይህ መጽሐፍ ለጦርነቱ “የኢትዮጵያና የጣሊያን ኹለተኛው ጦርነት” የሚል መጠርያን ሰጥቶታል፡፡ ጦርነቱን “ከአድዋው ጦርነት” ለይቶ ለመጥራት “የማይጨው ጦርነት” ሲባል የኖረ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ጦርነቱ ማይጨው ላይ ብቻ የተደረገ ሊያስመስለው ችሏል፡፡ ስለዚህ “ኹለተኛው የኢትዮጵያ- ጣሊያን ጦርነት ጥሩ መለያ ነው፡፡ ግልጽም ነው፤ በ1888 የተደረገው ጦርነት አንደኛ፣ ከ1927 እስከ 1933 ድረስ የነበረው ይኸኛው ደግሞ ኹለተኛው፡፡
ነገር ግን እንዲህ በቁጥር ሲለይ አብሮ መታየት የሚገባው ሌሎች ጦርነቶች የነበሩ መኾኑን ማሳጣት የለበትም፡፡ ኢትዮጵያ ከሮማውያን ጋር ያደረገቻቸውን ጦርነቶች ምሁራዊው ዓለም ባያጤነውም  ከእነአካቴው እንዳልተፈጸሙና የሌሉ አድርጎ ቢተዋቸውም፣ ለዘላለሙ እንዳይቆፈርና እንዳይወጣ፤ ራሱን የቻለ ተጨማሪ አትሞ መዝጊያ እስካልኾነ ድረስ ይህ ስያሜ አያነጋግርም፡፡ (ሮማ ዓለምን በመላ በመያዝ የዓለማቱ ኃያል መንግሥት በነበረችባቸው የጥንት ዘመኖቿ ውስጥ፣ በተለያዩ አቅጣጫዎች በተደጋጋሚ ከኢትዮጵያውያን ጋር ተዋግታለች፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ ያሉ ምሑራንና ተመራማሪዎች ጽሑፍ በሚቀርብበት የአካዳሚክ ዶት ኢዲዩ (Academic.edu) መካነ ድር፤ እንዲኹም፣ የጥንት ክት ሥራዎች መጽሔት በኾነው በኮሎራዶው ዩኒቨርሲቲ ክላሲክ አንቲክ ጆርናል በፈረንጆች 2013፣ በዲ-ሴልደን (ፕሮፌሰር) የቀረበው “ሃው ዘ ኢትዮጵያን ቼንጅ ሂዝ ስኪን” የተባለው የምርምር ሥራ ይህንኑ ይጠቁማል፡፡ “በግብፅ ፈርዖናዊ እና ከሮማዊው ወረራና ጥቃት” ኢትዮጵያውያን ራሳቸውን ጠብቀው፣ የደረሱባቸውን መክተው እያጠቁና እየረቱ የኖሩ መኾናቸውን ሲገልፅ በራሱ በቄሳር አውግስጦስ “ጌስቴው” ሳይቀር የተጠቀሰ ውጊያ እንደነበረ ይጠቁማል፡፡ በእንደነ ፕሊኒ ዓይነቱ የሮማን ዘመን ታሪክና መልክዓ ምድር ጸሐፊዎችም ያነሳሱት እንደኾነ ይገልጻል፡፡
በሌላ በኩል፣ አሜሪትስ- አንድ ዐይናዋ ሕንደኬ ታሪክ ላይም የሮማን ቄሳራዊ ጦር መግጠምዋ፣ የሮማን አዛዦች ሳይቀር እንዳስደነቀች ይነገራል፡፡ እንደነዚህ ዓይነቶቹ ተለቅመው በዘመን ቅደም ተከተል ቢደረደሩ ኢትዮጵያ ከሮም/ ጣሊያን ጋር ኹለቴ ብቻ በጦር ሜዳ እንዳልተሰለፈች ያሳውቃሉ፡፡ ከኹሉም በላይ፣ እነዚህን ታላላቅና ታናናሽ ዓውደ ውጊያዎች የሚገልጹት ግን የኢትዮጵያ የታሪክ ትውፊቶች ናቸው፡፡ በጥንቲቱ የንግሥና ሥርዓት መንግሥት መፈጸሚያ ከተማ፣ ከፓታ የተገኙት የኑቢያ ሠነዶች ይህን በየዘመኑ አቅርበዋል፡፡ እነዚህም በሌሎች የታሪክና አርኬዎሎጂዎች ግኝት ሊረጋገጡ የሚችሉ ናቸው፡፡ እንግዲህ እነዚያን ጦርነቶች ለዘላለሙ ድፍንፍን አድርጎ በማተም የሚያጠፋቸው እስካልኾነ ድረስ “ኹለተኛ” መባሉ አይከፋም፡፡ (ሮማንና ኢጣሊያን አንለይም ካልተባለ፡፡)
*    *    *
መጽሐፉ ከጦርነቱ አስቀድሞ የነበረውን የኢትዮጵያ የዓለም አጠቃላይ ኹኔታ፣ በተለይም የኢትዮ-ጣሊያንን ጨምሮ ከኹለተኛው የዓለም ጦርነት ጋር የሚሰናሰሉ ጉዳዮችን በመግለጥ ይጀምራል፡፡ በቀዳሚው ምዕራፍ አርበኛና አርበኝነት የተባሉትን ቃሎችና ጽንሰ ሐሳቦች በመፍታትና በመተርጎም መጀመሩ የመጽሐፉን ጥልቀት ገና ከወዲሁ ያመለክተናል፡፡ በየዘመኑና  በየፖለቲካዊ ፍላጎት እነዚህ ቃላት ልዩ ልዩ ኮነው ይያዛሉ፡፡ ከነበረው ብሔራዊ (ሀገራዊ) ትውፊት የወጣ አዲስ ዜግነት ለመፍጠር አስፈላጊ ኾኖ በተጀመረው የ“ሲቪክስ” ትምህርት “(ለማንኛውም ነገር) የሚኖር አለቅጥ የበዛ ፍቅር” ተብሎ የተፈታው አርበኝነት፤ በጦርነቱ ወቅት ለጣልያኖቹ ሽፍትነት ነበረ፡፡ “ከ1966 ዓመጽ (አብዮት) በኋላ ደግሞ ከደፈጣ ውጊያ ጋር” እንደተተነተነ በመጠቆም፣ እንደምን ኾኖ የታሪኩን ግንዛቤያችንን ሊያስለውጥ እንደቻለ ያስረዳል፡፡
“የአርበኝነቱ ጦርነት ያለ መንግሥት መሪነት፣ ሕዝብ በየመንደሩ እየተሰበሰበ ያካሔደው ዓመጽ ተደርጎ ተተርጉሟል፡፡ የግራ ዘመም ኮሚኒስት አብዮተኞች በቬትናም በኋላም በእነቼጎቬራ ከተካሔዱ ዓመጾች ጋር በማመሳሰል ለመተርጎም ሞክረዋል፡፡” (ገጽ 22)
“ለሀገር ህልውና፣ ለሥርዓት፣ ለኑሮው ዘይቤ የሚደረገውን” ጦርነት በዚያ ዘመን ሠርጾ ከነበረ ፀረ ቅኝ አገዛዝና ፀረ ፋሽስት እንዲኹም በየሀገሩ ከነበረው ከጨቋኝና ተራማጅ ካልተባሉ ገዥዎች ጋር ኹሉ ያለ የቅዋሜ ስሜትና ትግል ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ይህን የመሰለ “አብዮታዊ አተረጓጎም” መስጠቱ የነበረውን የአርበኝነት እንቅስቃሴ ጣሊያኖች ይከራከሩበት ከነበረው ሐሳብ ጋር ሠምሮ እስከመገኘት ድረስ አድርሷል፡፡ በአምስት ዓመቱ ውስጥም፤ በኢትዮጵያ የጣሊያን አስተዳደር በከተሞችና ጥቂት መንደሮች ላይ ብቻ ካልኾነ በሰፊው የሀገሪቱ ክፍል ፈጽሞ ያልሠፈነ እንደነበረ ከሚገለጸው ጋር የሚጣላና ጣሊያንም በዓለም ዓቀፍ መድረክ ትሟገትበት በነበረው አገነዛዘብ ተስተካክሎ እስከ መገኘት ድረስ የሚታይ አተረጓጎም ይኾናል፡፡ ይልቁንም፣ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ይህን ቃል/ ጽንሰ ሐሳብ የመግለጹ አላስፈላጊነት የሚታየው የንጉሠ ነገሥቱን አርበኝነት ለመናገርም ማስቻሉ ነው፡፡
ይኼው ጦርነት በአርበኝነት ውስጥ ኹለት የአርበኝነት ዓይነቶች የተፈጠሩበትና የታዩበት መኾኑንም፣ “የጦርነቱ ሒደት የፈጠራቸው አዳዲስ ጽንሰ ሐሳቦች” በሚለው ንዑስ ርእስ ሥር ይቆጠራሉ። ቀድሞም ከነበረው “ተጋዳይ አርበኛ” ሌላ “የውስጥ አርበኛ” እና “የስደት ተሟጋች አርበኛ” የተባሉ የአርበኝነት ዓይነቶችን ይጠቅሳሉ - ጸሐፊው፡፡
በኢትዮጵያውን ዘንድ የነበረው “ወራሪዎችን የመዋጋትና የመቋቋም ልምድ ቻይናውያን እንዲቀስሙ” ማኦሴቱንግ ሕዝባቸውን ወይም ሕዝባዊ ቀይ ጦራቸውን ሲመክሩ እንደነበረም በዚኹ መጽሐፍ ውስጥ እናገኛለን። ከጦርነቱ ቀደም ብሎ የነበረው የዓለም ኹኔታ ተብለው የሚገለጹት ከአንደኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የተፈጠረው የየመንግሥታቱ አወጋገን፣ ከዚያ ጦርነት በኋላ የተፈጠረው የዓለም መንግሥታት ማኅበር (ሊግ ኦፍ ኔሽን” ይባል የነበረው) እና አሠራሩ የመሳሰሉት ኹሉ ከዚኹ ጦርነት ጋር የሚያያዙበት ስላላቸው ነው፡፡ ይልቁንም ደግሞ፣ ጦርነቱ በኋላ በየሀገራቱ መንግሥታት (በአሸናፊውና በተሸናፊው) ይደረጉ የነበሩት ውሎችና አፈጻጸማቸው ላይ እንደ መሠረተ ሐሳብ የተያዙት፣ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ውድሮው ዊልሰን እና የሶቭየት ኅብረቱ ቭላድሚር ኢልይች ሌኒን “የራስን ዕድል በራስ የመወሰን” እሳቤዎች፣ ከጦርነቱ በፊት የኢትዮጵያን መንግሥት ማዳከምያ ፕሮፓጋንዳ ኾኖ እንደቆየ፣ ጥላሁን ይገልጹልናል፡፡
ይህን እሳቤ የኹለቱ ሀገር መሪዎች ከተለያየ ጥያቄና መነሻ ፍላጎታቸው የተነሳ ነበር ያቀነቀኗቸው። በአንደኛው ዓለም ጦርነት ወቅት አሜሪካ በዓለም ላይ ልቃና በልጽጋ ብቅ ያለችበት ጊዜ ነበር፡፡ የዚያን ጊዜዋ አውሮፓ በጦርነትና በአብዮቶች ትተረማመስ ነበር። የመጀመርያው የዓለም ጦርነት ፍትሐዊ መርሕ ላይ በተመሠረተ ስምምነት ጦርነቱ እንዲዘጋ ሩስያ ጥሪ አደረገች፡፡ ይህንን በመያዝ፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ድሮው ዊልሰን “በአውሮፓ የተያዙት ግዛቶችን ቅድሚያ ከአውሮፓውያን እጅ ውጭ ማድረግ ስላለባቸው” አጋርነታቸውን በነፃነት ቢወስኑ ለአሜሪካ ወዳጅ ይኾናሉ በማለት “የራስን ዕድል በራስ” አለ፤ የሩስያው ሌኒናዊ ኮሚኒዝም “ዓለም የወዛደሮች ትኾናለች” በሚል ሕልም (ወታደራዊ ዓለም አቀፋዊነት) በአንድ ኮሚዩኒስታዊ ፓርቲ ሥር በማደራጀት የጀመረውን አብዮት በመላው ዓለም ለማድረስ ሲል፣ “የብሔር ጥያቄ” የሚል መፍትሔ ይዞ ተነሳ፡፡ (በኹለተኛው የዓለም ጦርነት ዘመን የነበረችው ሶቭየት ኅብረት በሩሲያ ዙርያ ያሉ ሀገሮችን በኅብረቱ ውስጥ ለመቀላቀል ሲል ስታሊን አጥብቆ ያቀነቅነው ስለነበረ ብዙውን ጊዜ ይህ “የብሔር ጥያቄ” የተባለው ሐሳብ፤ ከእርሱ ጋር ተያይዞ፣በተለይ በኛይቱ ሀገር ሲገለጽና ሲተነተን እናገኘዋለን፡፡)
*     *     *
ስለ ጦርነቱ ጠቅላይ አዛዥ ስለ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ያለውን ከጦርነቱ ጋር የተያያዘ ግንዛቤ እናውቀዋለን፡፡ “ማይጨው ላይ አንድ መድፍ ተደግፎ ፎቶ ተነሳ” ይላሉ ፕሮፌሰር መስፍን ወ/ማርያም፡፡ ከዚያ ሸሽተው፣ በስደት እንግሊዝ ቆዩ፤ ከአምስት ዓመት በኋላ በኦሜድላ በበላያ በኩል አድርገው፣ ሚያዝያ 27ቀን 1933 አዲስ አበባ ገቡ፡፡ እሳቸው የገቡበት ቀንም የነፃነት ቀን ተብሎ ይከበራል፡፡
ይህ ነው እንግዲህ በትንሽ ትልቁ የሚታወቀው የንጉሠ ነገሥቱ የጦርነት ታሪክ፡፡ ብዙ ታሪኮችም፣ የታሪክ መምህራንና ጸሐፊዎችም የሚያጎሉት ጉዳይ ነው። የጥላሁን ጣሰው የጦርነቱ ታሪክ ውስጥ ግን የንጉሠ ነገሥቱ ታላቅ የጦር መሪነት በተጨባጭ ጎልቶ ይታያል። ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን እንደ ጠቅላይ አዛዥ የጦር መሪ ለመመልከትና ለመያዝ ያልተቻለበትን ምክንያት ሲያስቡት በውኑ ራስን በጥያቄ ማዕበል ማንገላታት ብቻ ነው የሚተርፈው፡፡ ግራ አጋቢ ነው! ይህ መጽሐፍ ነው እንዲህ ባለ ጥያቄ ውስጥም የሚያስገባዎት! ንጉሠ ነገሥቱ በእርግጥም የዚያ ጦርነት ጠቅላይ አዛዥ ነበሩ፡፡ ይህን ጦርነት ከአዲስ አበባ ሳይነሱ ጀምሮ፣ ማይጨው ላይም የጦርነቱ መሪ ወይም የጦሩ ጠቅላይ አዛዥ እንደነበሩ የሚያዩበት መጽሐፍ ነው፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ ወደ ውጭ ከወጡ በኋላ በየገጠሩ፣ በየቀበሌው፣ በየጎበዝ አለቃው እየተሰባሰበ በያለበት በእንቢተኝነት እንዲተጋተግ ለማሳመን የባተሉት ጣሊያኖች እንደነበሩ በማስረጃ አስደግፈው ያቀርቡልናል፡፡ ንጉሡ ሸሽቶ ፈረጠጠ ማስባሉም ቢኾን የጣሊያኖች መቀስቀሻ እንደነበረ ተወስቷል፡፡ እነዚህኑ በመቀበል ይዘን እንደኖርንም ጭምር፡፡
በዚህ በመጨረሻው የኢትዮ ጣሊያን ጦርነት፣ በየትኛውም ጦርነት ያልተገኘ ጥቅምና ውጤት ለኢትዮጵያ እንደተገኘም ነው ጥላሁን የጻፉት፡፡ መልካም ውጤቶች ያሏቸውንም ይቆጥሩልናል፡-
“ከመረብ ወዲህና ወዲያ ማዶ” ተለያይተው የነበሩት ሕዝቦቿ ተዋሃዱ፤የኤርትራና የቀሪው ኢትዮጵያ ጸረ ፋሺስት ታጋዮች በኀብረት ቆሙ፤
ኢትዮጵያ ትመኝ የነበረውን የባህር በር ባለቤትነት አሳካች፤
በሺ ኪ. ሜትር የሚቆጠር የባሕር ጠረፍ ድንበር ባለቤት ኾነች፡፡ (ገጽ 14)
ከነዚህም ሌላ ከጦርነቱ ፍጻሜ በኋላ ኢትዮጵያ የተባበሩ መንግሥታት ድርጅትን ለመመሥረት ከበቁት ሀገሮች አንደኛዋ ኾናለች፡፡ የአፍሪካ ነፃነት እውን እንዲኾንም የጦርነቱ ውጤት ግፊት አድርጓል፡፡ (ገጽ 14)
የጥላሁን ጣሰው የጦርነቱ ታሪክ መጽሐፍ ከሚተርክልን በተጨማሪ የዚህን የጦርነት ታሪክ ዘመን፣ ከኅዳር 27 ቀን 1927 ዓ.ም ጀምሮ፣ ከጦርነቱ በኋላ በ1934 ዓ.ም ጥር 23 ከእንግሊዝ መንግስት ጋር የስምምነት ውል እስከተፈረመበት ዕለት ድረስ ያሉትን፣ በዓመት፣ ወርና ቀን ቅደም ተከተል የደረደረልንም መጽሐፍ ነው፡፡ በወቅቱ ፖለቲካዊ ካርቱን ያቀርብ የነበረው ዴቪድ ሎው፣ በሞሶሊኒና በሊጉ ይዘብትባቸው የነበሩትን ጨምሮ በርካታ ፎቶዎችም ተካትተውበታል። ብዙውን ጊዜ በመሰል ታሪክ ጸሐፊዎች (በአማርኛ) ዘንድ የማያጋጥመን የፊደል ተራ ማውጫም ያለው መጽሐፍ ነው፡፡
በአጠቃላይ ስለ ጦርነቱ እስከ ዛሬ ብዙ መጻሕፍት የቀረቡልን ቢመስልም፣ በተሟላ መጠን የቀረበበት ግን ይሄው የጥላሁን ጣሰው መጽሀፍ ነው ብለን ለመናገር ያስደፍረናል፡፡ ራሳቸው አስቀድመው እንደገለጹትም፤ስለ ጦርነቱ ለታሪክ ተመራማሪዎችና መርማሪዎችም ብሔራዊ አተረጓጎም እስከ መሆን ድረስ የበቃ ነው፡፡

• “...lead us not into temptation” የሚለው አባባል ስህተት ነው ብለዋል።
      • በአማርኛ ሕትመቶች፣ “ወደ ፈተና አታግባን” ተብሎ እንደተተረጎመ ይታወቃል።

   አባታችን ሆይ ተብሎ የሚታወቀው ፀሎት እንዲሻሻል እንደሚፈልጉ የካቶሊክ ቤተክርስትያን ፓትርያርክ ፍራንሲስ፣ ለሮይተርስ ተናገሩ። “አባታችን ሆይ”፣ የዘወትር ፀሎት እንደሆነ በብዙዎች እንደሚታመንበት ሮይተርስ ጠቅሶ፣ በዚሁ ፀሎት ውስጥ፣ “...lead us not into temptation” የሚለው አባባል ስህተት እንደሆነ ፓትርያኩ አባ ፍራንሲስ እንደተናገሩ ትናንት ዘግቧል።
King James Version (KJV) ተብሎ በሚታወቀው ትርጉም ላይ “...lead us not into temptation” በሚል አገላለፅ ተተርጉሟል። ወደ ፈተና አትምራን እንደማለት ነው።
American Standard Version (ASV) ተብሎ በሚታወቀው ትርጉም ላይ ደግሞ “...bring us not into temptation” በሚል አገላለፅ ሰፍሯል። ወደ ፈተና አታድርሰን፣ ወደ ፈተና አታቅርበን፣ ወደ ፈተና አታስገባን... የሚል ተመሳሳይ ትርጉም የያዘ ነው።
ፓትርያርኩ አባ ፍራንሲስ፣ እነዚህ አባባሎች፣ በተሳሳተ አተረጓጎም ሳቢያ የተዛባ መልዕክት ያዘሉ ናቸው ብለዋል። ፈጣሪ ለፈተና ይዳርገናል የሚል የተዛባ መልዕክት የያዙ የተሳሳቱ አተረጓጎሞች እንዲስተካከሉ እፈልጋለሁ ሲሉም ተናግረዋል - ጳጳሱ። “...let us not into temptation” በሚል አባባል መስተካከል እንዳለባቸውም ጳጳሱ ገልፀዋል። ይህ አባባል፣ ከቀድሞዎቹ የእንግሊዝኛ ትርጉሞች የተለየ መልዕክት የያዘ እንደሆነ ተናግረዋል። ለፈተና አታጋልጠን፣ ከፈተና ጠብቀን፣ ከፈተና ከልለን አይነት መልእክት ይመስላል አተረጓጎሙ። እነዚህ አባባሎች፣ ከቀድሞው የአማርኛ ትርጉም፣ (ወደ ፈተና አታግባን ከሚለው አባባል) ጋር፣ የዚያን ያህል የተራራቀ መልዕክት ይዘዋል ለማለት ግን አስቸጋሪ ነው (... ወደ ፈተና አታስገባን... ከማለት ይልቅ... ወደ ፈተና አታግባን ተብሎ የተተረጎመ ከመሆኑ አንፃር)።
አባታችን ሆይ የሚለው ፀሎት በክርስትና መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ፣ በሁለት ቦታዎች የሰፈረ መሆኑን ዘገባዎቹ አያይዘው ገልፀዋል።
ማትዮስ 6፡9-13 የሰፈረው ፅሁፍ የመጀመሪያው ሲሆን፣ እንዲህ ይላል።
በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፣  ስምህ ይቀደስ፣ መንግስትህ ትምጣ፤
ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን፤
የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን፤
እኛም ደግሞ የበደሉንን ይቅር እንደምንል፣ በደላችንን ይቅር በለን፤
ከክፉም አድነን እንጂ፣ ወደ ፈተና አታግባን፤ መንግስት ያንተ ናትና ኃይልም ክብርም ለዘለዓለሙ፤ አሜን።
ሁለተኛውና አጠር ብሎ የቀረበው ደግሞ በሉቃስ ወንጌል የተፃፈው ነው።
ሉቃስ 11፡2-4
በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፣  ስምህ ይቀደስ፣ መንግስትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች፣ እንዲሁ በምድር ትሁን፤
የዕለት እንጀራችንን ዕለት በዕለት ስጠን፤
ኃጢአታችንንም ይቅር በለን፣ እኛ ደግሞ የበደሉንን ሁሉ ይቅር ብለናልና፤ ከክፉም አድነን እንጂ፣ ወደ ፈተና አታግባን።