Administrator

Administrator

Sunday, 19 February 2017 00:00

የፍቅር ጥግ

 - አንገቴ ላይ አልማዝ ከማጠልቅ ይልቅ ጠረጴዛዬ ላይ ፅጌረዳ ቢኖር እመርጣለሁ፡፡
  ኢማ ጎልድማን
- ሽቶና አበቦችን እወዳለሁ፡፡
  ዶናቴላ ቨርሳቼ
- መፋቀር እርስ በርስ መተያየት ብቻ አይደለም፤ ወደ ተመሳሳይ አቅጣጫ መመልከትም ነው፡፡
  አንቶይኔ ዲ ሴይንት ኤክሱፔሪ
- ፍቅር የዳበሰው ሰው በጨለማ ውስጥ አይጓዝም፡፡
  ፕሌቶ
- ፍቅር ቀድሞ ያልነበሩ በሮችንና መስኮቶችንም እንኳን ያስከፍታል፡፡
  ሚኞን ማክላውግህሊን
- ለአንቺ ያለኝን ፍቅር በሙሉ ለመሸከም መቶ ልቦች በጣም ያንሳሉ፡፡
  ያልታወቀ ደራሲ
- ፍቅር ሁለት ሰዎች የሚጫወቱትና ሁለቱም የሚያሸንፉበት ጨዋታ ነው፡፡
  ኢቫ ጋቦር
- ፍቅር የስሜቶቻችን ግጥም ነው፡፡
  ሆኖሬ ዲ. ባልዛክ
- ነይና ልቤ ውስጥ ኑሪ፤ ኪራይ አትከፍይም፡፡
  ሳሙኤል ላቨር
- አፍቅሪኝ፤ ያኔ ዓለም የእኔ ትሆናለች፡፡
  ዴቪድ ሪድ
- ፍቅር ማለት አብሮ መጃጃል ነው፡፡
  ፓውል ቫለሪ
- ሰዎች ስለወደዱን ብቻ ለምን ጅሎች ናቸው ብለን እናስባለን?
  ኤማ አታ አይዱ
- እግዚአብሔር ፍቅር ነው፡፡ ይሄ ነው የህንድ የመጨረሻ መልዕክት
  ኢ.ኤም. ፎ ርስተር
- ፍቅር ለየት ያለ በሽታ መሆኑን ሁሉም ሰው ማወቅ አለበት፡፡
  ደብሊው.ሲ.ሃንዲ
- ፍቅር ምስጢር መሆኑ ያበቃ ዕለት፣ ደስታነቱ ያከትማል፡፡
  አፍራ ቤህን
- ፍቅር ልክ እንደ ኩፍኝ ሁላችንም ሊወጣልን ይገባል፡፡
  ጄሮሜ ኬ. ጄሮሜ

Sunday, 19 February 2017 00:00

የትምህርት ጥግ

 - ትምህርት የመጪው ዘመን ፓስፖርት ነው፤ ነገ ዛሬ ለተዘጋጁበት ናትና፡፡
   ማልኮም ኤክስ
- ትምህርት ለህይወት ዝግጅት የሚደረግበት አይደለም፤ ትምህርት ራሱ ህይወት ነው፡፡
  ጆን ዴዌይ
- ትምህርት የሚባለው፣ አንድ ሰው በት/ቤት የተማረውን ሲረሳ የሚቀረው ነው፡፡
  አልበርት አንስታይን
- የመማር ፍቅር አዳብር፡፡ ያንን ካደረግህ ጨርሶ ማደግ አታቆምም፡፡
  አንቶኒ ጄ. ዲ አንጄሎ
- ትምህርት የነፃነትን ወርቃማ በር መክፈቺያ ቁልፍ ነው፡፡
  ጆርጅ ዋሺንግተን ካርቨር
- የትምህርት ግብ፤ዕውቀትን ማሳደግና እውነትን ማሰራጨት ነው፡፡
  ጆን ኤፍ.ኬኔዲ
- የትክክለኛ ትምህርት የመጨረሻው ውጤት ለውጥ ማምጣት ነው፡፡
  ሊዮ ቡስካግሊያ
- ሀሳብን ባይቀበሉትም እንኳ ማስተናገድ የተማረ አዕምሮ መለያ ነው፡፡
  አሪስቶትል
- ትምህርት ሥራን ብቻ አይደለም ማስተማር ያለበት፤ ህይወትንም ማስተማር አለበት፡፡
  ደብሊው ኢ.ቢ.ዱ ቦይስ
- ከመምህሩ የማይበልጥ ተማሪ ደካማ ነው፡፡
  ሊዎናርዶ ዳ ቪንቺ
- የት/ቤትን በር የሚከፍት፣ የወህኒ ቤትን በር ይዘጋል፡፡
  ቪክቶር ሁጎ
- ማስተማር ማለት፤ ሁለቴ መማር ነው፡፡
  ጆሴፍ ጆውበርት
- የሁላችንም - ወንዶችም ሴቶችም፤ የመጀመሪያ ችግራችን አለመማራችን አይደለም፤ ከተማርነው መላቀቅ አለመቻላችን እንጂ፡፡
  ግሎሪያ ስቴይኔም
- የትምህርት ዘጠኝ አስረኛው ማነቃቃት ነው፡፡
  አናቶሌ ፍራንስ
- ትምህርት ውድ ነው ብለህ ካሰብክ፣ ድንቁርናን ሞክረው፡፡
  የቻይናውያን አባባል
- ህፃናት መማር ያለባቸው ምን እንደሚያስቡ ሳይሆን እንዴት እንደሚያስቡ ነው፡፡
  ማርጋሬት ሚድ
- ልብን ሳያስተምሩ አዕምሮን ማስተማር ጨርሶ ትምህርት አይባልም፡፡
  አሪስቶትል
- በቀላሉ ልትገልፀው ካልቻልክ፣ በቅጡ አልተረዳኸውም ማለት ነው፡፡
  አልበርት አንስታይን
- ትምህርት ማንም የማይነጥቅህ ሃብትህ ነው።
  የአሜሪካውያን አባባል

Sunday, 19 February 2017 00:00

የፀሀፍት ጥግ

 · የሥነ ፅሁፍ ማሽቆልቆል የአገር ማሽቆልቆልን ይጠቁማል፡፡
  ጆሃን ዎልፍጋንግ ቮን ገተ
· የእያንዳንዱ ሰው ትውስታ፣ የራሱ የግል ሥነ ፅሁፍ ነው፡፡
  አልዶዩስ ሃክስሌይ
· ሥነ ፅሁፍ የበለጠ የሚያብበው ግማሽ ንግድ፣ ግማሽ ጥበብ ሲሆን ነው፡፡
  ዊልያም ራልፍ ኢንግ
· የሥነ ፅሁፍ ዘውድ ሥነ ግጥም ነው፡፡
  ደብሊው ሶመርሴት ሟም
· በጃፓን ሥነ ፅሁፍ የተከተልኳቸው አርአያዎች የሉኝም፡፡ የራሴን ዘይቤ፣ የራሴን መንገድ ነው የፈጠርኩት፡፡
  ሀሩኪ ሙራካሚ
· ወደ ለንደን የሄድኩት የሥነ ፅሁፍ ምንጭ ስለሆነ ነው፡፡ እዚያ የሄድኩት በዲከንስና በሼክስፒር የተነሳ ነው፡፡
  ቤን ኦክሪ
· መፅሐፍ ደጋግመህ ልትገልጠው የምትችለው ስጦታ ነው፡፡
  ጋሪሶን ኬይሎር
· የሥነ ፅሁፍ ዓላማ ደምን ወደ ቀለም መለወጥ ነው፡፡
  ቲ.ኤስ.ኢሊዮት
· ከሥነ ፅሁፍ የምታገኘው መልስ በጠየቅኸው ጥያቄ ይወሰናል፡፡
  ማርጋሬት አትውድ
· ሁሉም ሥነ ፅሁፍ ሃሜት ነው፡፡
  ትሩማን ካፖቴ
· በቦስኒያ፤ ልቦለድና ኢ-ልቦለድ የሚባል ልዩነት የለም፤ ያንን የሚገልፅም ቃል የላቸውም፡፡
  አሌክሳንደር ሄሞን
· ልብ ወለድ በውሸት ውስጥ ያለ እውነት ነው፡፡
  ስቲፈን ኪንግ
· አንብብ፡፡ ስለ መፃህፍት የተነገሩህን ነገሮ በሙሉ እርሳና አንብብ፡፡
  ፓውሎ ኮልሆ
· ያነበብኳቸው ነገሮች ሁሉ አካል ነኝ፡፡
  ቴዎዶር ሩስቬልት
· ልትፅፈው ያልቻለችውን ግጥም ትኖረዋለች፡፡
  ኦስካር ዋይልድ
· እኔ ማለት መፅሀፍ በመጠጣት የምሰክር ሰው ነኝ፡፡
  ኤል.ኤም.ሞንትጎሜሪ

አንዳንድ ጨዋታ የዕውነት ያህል አሳማኝ ነው፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን በተባበሩት መንግሥታት ጉባዔ ላይ ከፍተኛ ጭቅጭቅ ይነሳል፡፡ በኃይል ጭቅጭቁን ያካረሩት አራት አገሮች ናቸው፡-
1ኛ/ እንግሊዝ
2ኛ/ ፈረንሣይ
3ኛ/ እሥራኤል
4ኛ/ ሩማኒያ
እንዲያ በኃይል ያጨቃጨቃቸው አጀንዳ፤ “አዳምና ሔዋን የየት አገር ሰዎች ናቸው?” የሚለው ጉዳይ ነው፡፡
በመጀመሪያ ሙግቷን ያቀረበችው እንግሊዝ ናት፡፡ እንዲህ ነው ያለችው፤ በተወካይዋ አማካኝነት፤
“አዳምና ሔዋን ያለጥርጥር እንግሊዞች ናቸው፡፡ ለምን ቢባል፤ እንግሊዛዊ ሰው ብቻ ነው አንዲት ሴት ትፈጠር ዘንድ በጨዋነት የገዛ ጎድኑን አሳልፎ የሚሰጥ”  
ይሄኔ የፈረንሳዩ ተወካይ ከመቀመጫው ተፈናጥሮ ተነሳና፤
“በጭራሽ እንደዛ አይሆንም! እስቲ የአዳምን ቁመናና ቁንጅና ተመልከቱ፡፡ ራቁቱን ሆኖ እንኳን እንዴት እንደሚያምር ልብ - በሉ፡፡ ይሄ ሊኖረው የሚችለው ፈረንሳዊ ብቻ ነው” አለ፡፡
ቀጥሎ የቀረበው ተሟጋች እሥራኤላዊው ተወካይ ነበር፡፡ እንዲህ አለ፡-
“በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ በትክክል እንደተቀመጠው፤ፍጥረት የተፈጠረው በቅድስቲቱ ምድር ነው፡፡ ስለዚህም አዳምና ሔዋን የተመረጡት ህዝቦች ናቸው! ስለሆነም አይሁዳውያን ናቸው!”
ይሄኔ የሩማኒያው ተወካይ ጭንቅላቱን እየነቀነቀ ብድግ አለና፤
“የለም! በእኛ በሩማንያን ዕምነት አዳምና ሔዋን ሊሆኑ የሚችሉት ሩሲያዊ ነው!”
“እንዴት? አስረዳና?” ብለው ሁሉም ጮሁበት፡፡
የሩማንያው ተወካይም፤
“ምክንያቴን ላቅርብላችሁ፡፡ በዓለም ላይ ሩሲያዊ ብቻ ነው በደንብ ሳይበላና በደምብ ሳይለብስ ገነት ውስጥ ነው ያለሁት የሚል!” ሲል ገለፀ፡፡
ተጨበጨበለት!!
*   *   *
አገርን ከሌላ አገር ማስበለጥ፣ የራስን ፓርቲ ከሌላው ፓርቲ የበላይ ነው ለማለት መሞከርና እኔ እሻል እኔ እሻል መባባል፣ ጥንትም ነበረ፣ አሁንም ያለ እና ወደፊትም የሚኖር ነው፡፡ ያም ሆኖ ያላንዳች ምክናዊነት፣ አንዱ ሌላውን መብለጥ አይችልም፡፡ አመክንዮ ይፈልጋል፡፡
በሀገር ደረጃ ሲታይ ከፖለቲካ ጥንካሬ እስከ ኢኮኖሚ ጥንካሬ፣ ከዚያም የወታደራዊ አቅም፣ እንዲሁም ማህበራዊ መሰረትን ይጠይቃል፡፡ እነዚህን ለማሟላት ብርቱ ድካም፣ የረዥም ጊዜ ባለታሪክ መሆንንም ይጠይቃል፡፡
በሀገራችን ያየናቸው ለውጦች ከወታደራዊ መፈንቅለ መንግስት፣ እስከ ተማሪ እንቅስቃሴ፣ ውለው አድረውም የተደራጁ ወታደራዊ ኃይሎች አመራር ሥር የወደቁ ነበሩ፡፡ በዚሁ ዙሪያ የተደራጁ ፓርቲዎችና ድርጅቶች ተወልደዋል፡፡ ወደ ትጥቅ ትግልም ያደጉ ታይተዋል፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ ግን እርስ በርስ ከመቆራቆስና ከመጠላለፍ፣ አልፎ ተርፎም ከመጨራረስ በስተቀር ሁነኛ የፖለቲካ መድረክ ፈጥረው፣ ሁነኛ ክርክርና ሀቀኛ ሙግት ተሟግተው፣ እዚህ ስምምነት ላይ ደረሱ የሚባልላቸውና የሚያኮሩ አልተገኙም፡፡ መንግሥትና ተቃዋሚ ፓርቲዎች፣አይጥና ድመት ዓይነት ሁኔታ ውስጥ ነበሩ፡፡ ክፍተቱ ሰፊ ነው፡፡ እስከ ዛሬ ስናይ የኖርነው፤ የቂም በቀል፣ የደባና የሤራ፣ ከእኔ በላይ ላሣር እና የደም መፈላለግ ፍጥጫ በመሆኑ የሰላማዊ ትግል ጠረጴዛ ላይ ተቀምጦ፣በሰለጠነ መልክ ተነጋግሮ ዳር መድረስ ያልተሞከረ ነው፡፡ አንድ ፀሐፊ እንዳለው፤ “የኢትዮጵያ ፖለቲከኛ ሁሉ በየኪሱ ትናንሽ ዘውድ ይዞ ነው የሚዞረው!”
ከተማሪ እንቅስቃሴ ጊዜ ጀምሮ እንደመሪ መፈክር ሲያገለግል የኖረው፤   
‹‹unity is power››
‹‹አንድነት ኃይል ነው›› የሚል ነበር፡፡
“United, we stand
 Separated, we fall!›› የሚልም ነበር፡፡ (‹‹ከተባበርን እንቆማለን፤ከተነጣጠልን እንወድቃለን!›› እንደ ማለት ነው፡፡) በአጭሩና በተለመደው የአማርኛ አባባል፤‹‹ድር ቢያብር አንበሳ ያሥር›› ማለት ነው፡፡ ይሄ ዛሬም ይሠራል፤በአግባቡ የሚጠቀምበት ከተገኘ፡፡ ጥበብ ይጠይቃል፡፡ በሆይ ሆይታና በግርግር፤ በችኮላ የሚፈጠር አካሄድ መጨረሻው አያምርም፡፡ የፖለቲካ ድርድር የአንድ ወገን ብልጠት አይደለም፡፡ የሀገር ጉዳይ ነውና ሁሉም ወገን በልባዊነት ሽንጡን ጠበቅ ሊያደርግበት የሚገባ ነገር ነው፡፡ በተንኮል ሽረባም የሚሆን ነገር አይደለም፡፡ ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን፤
‹‹ነገር በሆድ ማመቅ
ለትውልድ መርዝ መጥመቅ›› የሚለን ለዚህ ነው!
ከሁሉም በላይ መቻቻል የሚፈተንበት፣ሆደ-ሰፊውና አስተዋዩ የሚለይበት ነው። የፖለቲካ ብልህነት ጠርቶ የሚወጣበት ነው፡፡ ዲሞክራሲ የተሸናፊዎች መብት መሆኑን በእርግጥ የምናጣራበት ሂደትም ነው፡፡ ገዢው ዘራፍ ሳይል፣ተገዢው በቂምና በቅሬታ ሳይወጣ ማየት እንሻለን፡፡ ሰላማዊ ትግል የሰላም አገር መለያ ነውና፣ከትንቅንቁ ባሻገር ግልፅ ውይይት እንጠብቃለን፡፡ ስለታሰሩ የተቃዋሚ አባላት ምን ሀሳብ እንደሚነሳ ለመስማት እንጓጓለን፡፡ ስለምርጫ ህግጋት ለውጥ ምን እንደሚወሳ ለማዳመጥ እንተጋለን፡፡ በመጨረሻ ግን አንደበተ ርቱዕነት ብቻውን የአሸናፊነት መገለጫ እንዳልሆነ እናውቃለን፡፡ ቀናነት፣ ቁጡነትን ማስወገድ፣ የቤት ሥራን በሚገባ ሰርቶ መምጣት፣ ወቅታዊ (timely) የሆነውን ጉዳይ፤ ጊዜ ከማይሽረው (timeless) ጉዳይ ለይቶ ማየት ወሳኝነት አላቸው፡፡ ከሁሉም በላይ ግን፤
‹‹በርበሬ አይሆንም ዕጣን
ንግግር አይሆንም ሥልጣን››
የሚለውን አባባል አለመዘንጋት ነው! ይሄን ልብ እንዲሉም አደራ ጭምር እናስታውሳለን፡፡

ከአፍሪካ እና የመካከለኛው ምስራቅ አየር መንገዶች አንደኛ ደረጃን ይዟል

    የኢትዮጵያ አየር መንገድ የበረራ ሰዓትን በማክበር ከአለማችን አየር መንገዶች 11ኛ፣ ከአፍሪካና ከመካከለኛው ምስራቅ አገራት አየር መንገዶች ደግሞ የ1ኛ ደረጃን መያዙን አለማቀፉ የአቪየሽን የመረጃ ተቋም “ፍላይትስታትስ” ሰሞኑን ባወጣው ወርሃዊ አስታውቋል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በአዲሱ የፈረንጆች አመት 2017 የመጀመሪያ ወር ካደረጋቸው 8 ሺህ ያህል በረራዎች 81 በመቶ ያህሉን ያጠናቀቀው፣ በረራዎቹን ለማጠናቀቅ ካስቀመጠው ጊዜ በ15 ደቂቃዎች ውስጥ መሆኑንም ተቋሙ በመግለጫው ጠቅሷል፡፡
አየር መንገዱ በበረራ ሰዓት አክባሪነት በአለማቀፍ ደረጃ ባስመዘገበው ከፍተኛ ውጤት ጥልቅ ደስታ ተሰምቶናል፤ ስኬቱ የአየር መንገዳችን የ12 ሺህ ትጉህ ሰራተኞች ጥረት ውጤት በመሆኑ ‹እንኳን ደስ አላችሁ› ለማለት እወዳለሁ ብለዋል፤ ዋና ስራ አስፈጻሚው አቶ ተወልደ ገብረ መድህን፡፡
“ሰዓቱን የጠበቀ በረራ ማከናወን የክቡራን ደምበኞቻችንን ፍላጎት በአግባቡ ለማሟላት ወሳኝ መሆኑን በአግባቡ እንረዳለን፤ ሁላችንም ሰዓቱን የጠበቀ በረራ እንዲኖር ለማስቻል ተግተን እየሰራን ነው” ሲሉም አክለዋል፡፡

    የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማኅበር 25ኛ ዓመት የብር ኢዮበልዩ በዓሉን ያከበረ ሲሆን ማኅበሩ ስኬታማ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን የቦርድ ሊቀመንበሩ አሳታውቀዋል፡፡
ማኅበሩ 25ኛ የብር ኢዮበልዩ በዓሉንና ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤውን ከትናንት በስቲያ በሸራተን ሆቴል ባከበረበት ወቅት የቦርድ ሊቀመንበሩ ኢ/ር አበራ በቀለ፣ ከጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ ማኅበሩ ስኬታማ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው የአባሎቻቸው የመፈፀም አቅም እየጎለበተ የኮንትራት አስተዳደር፣ የሳይት ማኔጅመንትና የኩባንያ አደረጃጀት እየተሻሻለ መሆኑን ተናግረዋል።
ማኅበሩ ሲመሠረት የአባላት ቁጥር 30 እንደነበር የጠቀሱት ሊቀመንበሩ፣ በአሁኑ ወቅት የአባላት ቁጥር ከ1600 በላይ መድረሱን፣ ከአዲስ አበባ ውጭ በክልል ከተሞች በባህርዳር፣ በመቀሌና በሀዋሳ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች መክፈቱ የስኬታማነቱ መገለጫ ናቸው ብለዋል፡፡
አገሪቷ ባለፉት 25 ዓመታት ያከናወነቻቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች፣ የቤቶች ግንባታ፣ የመንገዶች፣ ድልድዮች፣ የኃይል ማመንጫ ግድቦች…. ፕሮጀክቶችና የአገር ውስጥ ኮንትራክተሮች አቅም አይመጣጠንም ያሉት ኢ/ር አበራ፤ ከመንግሥት ጋር በጣምራ በመሆን ኮንትራክተሮች ራሳቸውን የሚያደራጁበት የአቅም ግንባታ ሥራ ይጠብቀናል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
የፕሮጀክቶችን መጓተትና መዘግየት በተመለከተ ውጫዊና ውስጣዊ ምክንያቶች እንዳሉ ጠቅሰው፣ ውጫዊ የምንለው፣ ሥራው ለኮንትራክተሮች ሲሰጥ ፅድት ብሎ ተሰርቶ፣ ፕላኑ ፣ በጀቱ፣… ካልተሰጠ፣ ፕላኑ የሚቀየር፣ በጀቱ የሚቀነስ ከሆነ፣ ከሥራው ጋር ተያያዥነት ያላቸው ነገሮች ሥራ ካልተጠናቀቀ፣ ማለትም ሥራው ከመጀመሩ በፊት የተጠናቀቀ ዶክመንት ካልቀረበ  ፕሮጀክቱ ይጓተታል፡፡ ውስጣዊ ምክንያቶች የሚባሉት ደግሞ የኮንትራክተሩ የአቅም ማነስ ችግር ነው፤ በተለይ የፋይናንስ፡፡ “የኮንትራክተሩ ገንዘብ ያለው ሚክሰር፣ ገልባጭ፣ ዶዘር፣ የመሳሰሉት ላይ ስለሆነ ሥራ ማስኬጃ ያጥረዋል፤ ገንዘብ እስኪያገኝ ድረስ ሥራው ይዘገያል፣ ይጓተታል በማለት አስረድተዋል፡፡

በአውሮፓ ትልቁ የሆቴል ዘርፍ ኩባንያ የሆነው የፈረንሳዩ አኮር ሆቴልስ ግሩፕ በአዲስ አበባ ሶስት ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎችን ለመክፈት የሚያስችለውን የግንባታና የማኔጅመንት ስምምነት ከኢትዮጵያውያን ባለሃብቶች ጋር መፈጸሙን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ኩባንያው ባለፈው ረቡዕ ያወጣውን መግለጫ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በአዲስ አበባ ከተማ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገነቡት ሶስቱ ሆቴሎች እስከ መጪዎቹ አራት አመታት ጊዜ ውስጥ ግንባታቸው ተጠናቅቆ ስራ ይጀምራሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ ሆቴሎቹ በድምሩ 527 ያህል የመኝታ ክፍሎች ይኖሯቸዋል፡፡
ኩባንያው በአዲስ አበባ ከተባበሩት መንግስታት የአፍሪካ የኢኮኖሚ ኮሚሽን አቅራቢያ የሚከፍተውና 162 መኝታ ክፍሎች የሚኖሩት የመጀመሪያው ሆቴል በሶስት አመታት ውስጥ ተጠናቅቆ ስራ እንደሚጀምር የሚጠበቅ ሲሆን፣ በዚሁ አካባቢ የሚገነባውና 135 የመኝታ ክፍሎች የሚኖሩት ሁለተኛው ሆቴልም በሁለት አመታት ጊዜ ውስጥ እንደሚጠናቀቅ ተነግሯል፡፡
ከአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን አቅራቢያ የሚገነባውና እ.ኤ.አ በ2021 ግንባታው ተጠናቅቆ ስራ ይጀምራል ተብሎ የሚጠበቀው ሶስተኛው ሆቴል ደግሞ፣ 230 መኝታ ክፍሎች እና 22 ወለሎች እንደሚኖሩት ተገልጧል። አኮር ሄቴልስ ኩባንያ በአፍሪካ የሆቴል ኢንቨስትመንት ዘርፍ ከተሰማራ 40 አመታት ያህል እንደሆነው ያስታወሰው ሮይተርስ፤ በ21 የአፍሪካ አገራት በከፈታቸው 94 ሆቴሎች፤ ከ10 ሺህ በላይ ለሚሆኑ ሰዎች የስራ ዕድል መፍጠሩንም አክሎ ገልጧል፡፡

      የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማኅበር 25ኛ ዓመት የብር ኢዮበልዩ በዓሉን ያከበረ ሲሆን ማኅበሩ ስኬታማ ተግባራትን እያከናወነ መሆኑን የቦርድ ሊቀመንበሩ አሳታውቀዋል፡፡
ማኅበሩ 25ኛ የብር ኢዮበልዩ በዓሉንና ዓመታዊ ጠቅላላ ጉባኤውን ከትናንት በስቲያ በሸራተን ሆቴል ባከበረበት ወቅት የቦርድ ሊቀመንበሩ ኢ/ር አበራ በቀለ፣ ከጋዜጠኞች ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ ማኅበሩ ስኬታማ ተግባራት እያከናወነ መሆኑን ጠቅሰው የአባሎቻቸው የመፈፀም አቅም እየጎለበተ የኮንትራት አስተዳደር፣ የሳይት ማኔጅመንትና የኩባንያ አደረጃጀት እየተሻሻለ መሆኑን ተናግረዋል።
ማኅበሩ ሲመሠረት የአባላት ቁጥር 30 እንደነበር የጠቀሱት ሊቀመንበሩ፣ በአሁኑ ወቅት የአባላት ቁጥር ከ1600 በላይ መድረሱን፣ ከአዲስ አበባ ውጭ በክልል ከተሞች በባህርዳር፣ በመቀሌና በሀዋሳ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች መክፈቱ የስኬታማነቱ መገለጫ ናቸው ብለዋል፡፡
አገሪቷ ባለፉት 25 ዓመታት ያከናወነቻቸው ሜጋ ፕሮጀክቶች፣ የቤቶች ግንባታ፣ የመንገዶች፣ ድልድዮች፣ የኃይል ማመንጫ ግድቦች…. ፕሮጀክቶችና የአገር ውስጥ ኮንትራክተሮች አቅም አይመጣጠንም ያሉት ኢ/ር አበራ፤ ከመንግሥት ጋር በጣምራ በመሆን ኮንትራክተሮች ራሳቸውን የሚያደራጁበት የአቅም ግንባታ ሥራ ይጠብቀናል ሲሉ ገልጸዋል፡፡
የፕሮጀክቶችን መጓተትና መዘግየት በተመለከተ ውጫዊና ውስጣዊ ምክንያቶች እንዳሉ ጠቅሰው፣ ውጫዊ የምንለው፣ ሥራው ለኮንትራክተሮች ሲሰጥ ፅድት ብሎ ተሰርቶ፣ ፕላኑ ፣ በጀቱ፣… ካልተሰጠ፣ ፕላኑ የሚቀየር፣ በጀቱ የሚቀነስ ከሆነ፣ ከሥራው ጋር ተያያዥነት ያላቸው ነገሮች ሥራ ካልተጠናቀቀ፣ ማለትም ሥራው ከመጀመሩ በፊት የተጠናቀቀ ዶክመንት ካልቀረበ  ፕሮጀክቱ ይጓተታል፡፡ ውስጣዊ ምክንያቶች የሚባሉት ደግሞ የኮንትራክተሩ የአቅም ማነስ ችግር ነው፤ በተለይ የፋይናንስ፡፡ “የኮንትራክተሩ ገንዘብ ያለው ሚክሰር፣ ገልባጭ፣ ዶዘር፣ የመሳሰሉት ላይ ስለሆነ ሥራ ማስኬጃ ያጥረዋል፤ ገንዘብ እስኪያገኝ ድረስ ሥራው ይዘገያል፣ ይጓተታል በማለት አስረድተዋል፡፡

የደቡብ ኮርያ የጦር ሃይል አባላት የሆኑ ወታደሮች በኮርያ ዘመቻ ወቅት የተሳተፉና በጽናት በመታገል ታላቅ ውለታ የሰሩ ኢትዮጵያውያን ዘማቾችን ለመርዳት የሚውል የገንዘብ ድጋፍ እያሰባሰቡ እንደሚገኙ ተዘግቧል፡፡
የደቡብ ኮርያ ጦር በኦፊሻል የፌስቡክ ገጹ ላይ ያወጣውን መረጃ ጠቅሶ ኮፖጆላ የተባለው ድረገጽ ትናንት እንደዘገበው፣ የአገሪቱ 27ኛ ክፍለ ጦር አባላት የሆኑ ወታደሮች በአበል መልክ ከሚሰጣቸው ገንዘብ የተወሰነውን በማሰባሰብ በአለማቀፉ የእርዳታ ድርጅት በኩል ለኢትዮጵያውያን የኮርያ ዘማቾች ለመላክ እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡
እ.ኤ.አ በ1951 በተጀመረው የሁለቱ ኮርያዎች ጦርነት፣ ከ6 ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያን ዘማቾች ደቡብ ኮርያን በመደገፍ ለአምስት አመታት ያህል በጽናት መታገላቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ 122 ያህሉ ሲሞቱ 536 የሚሆኑት ደግሞ የመቁስል አደጋ እንደደረሰባቸው ገልጧል፡፡
ደቡብ ኮርያውያኑ ወታደሮች የሚያሰባስቡት ገንዘብ፣ በህይወት ለሚገኙ 350 ያህል ኢትዮጵያውያን ዘማቾች እንደሚደርስ የጠቆመው ዘገባው፣ ወታደሮቹ የኢትዮጵያውያን ዘማቾችን ፎቶግራፎች ይዘው በኩራት ስሜት ውለታቸውን እየዘከሩ የሚያሳየው ፎቶግራፍ፣ በጦሩ የፌስቡክ ድረገጽ ላይ መለቀቁንም አክሎ ገልጧል።

ለኦሮሚያ 2 ቢ ብር ተመድቧል - ከ1 ሚሊዮን በላይ ሰዎች ተጠቃሚ ይሆናሉ
 
ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ፤ በኦሮሚያ ስድስት ወረዳዎች የምግብ ዋስትናቸው ያልተረጋገጠ ከ1 ሚ. በላይ ሰዎችን ለመደገፍ የ2 ቢ. ብር
ፕሮጀክት ይፋ አደረገ፡፡ ባለፈው ሳምንት በአዳማ ከተማ አዩ ኢንተርናሽናል ሆቴል ይፋ ባደረገው በዚህ ፕሮጀክት ላይ፤ የክልሉ ኃላፊዎች፣ የወረዳ ተወካዮች፣ የወርልድ ቪዥን ካንትሪ ዳይሬክተሮችና ፕሮጀክት ማናጀሮች ተገኝተዋል፡፡ አምስት አመት የሚዘልቀው ይሄው ፕሮጀክት የሚተገበርበት ገንዘብ የተገኘው ዩስኤይድ ለዚሁ ተግባር ከመደበው 175 ሚሊዮን ዶላር ላይ እንደሆነ በዕለቱ ተነግሯል። ወርልድ ቪዥን ላለፉት 40 ዓመታት በኦሮሚያ ክልል 24 ወረዳዎችና አምስት ዞኖች የምግብ ዋስትና ድጋፍና ሌሎች የተቀናጁ የልማት ስራዎችን በመስራት ከ6 ሚ. በላይ ህፃናትንና በጣም ተጋላጭ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን ሲያገለግል መቆየቱም በዕለቱ ተገልጿል፡፡ ወርልድ ቪቪን ኢትዮጵያ ከዚህ ቀደም ባጠናቀቀው የአምስት አመት የልማትና የምግብ ድጋፍ ፕሮግራም ከ1.5 ሚ. በላይ ሰዎችን ተጠቃሚ ማድረጉን የገለፁት የኦሮሚያ ክልል የደህንነት፣ የግብርናና የተፈጥሮ ሀብት ምክትል ቢሮ ኃላፊ አቶ አንድነት ደገፋ አሁንም ወርልድ ቪዥን በ6 ወረዳዎች የምግብ የጤናና የመጠጥ ውሃ አቅርቦት ላይ ለመስራትና ወገኖችን ለመደገፍ ያቀረበውን ትልቅ ሀብት በአግባቡ መጠቀም አለብን ሲሉ ተናግረዋል፡፡የወርልድ ቪዥን የልማትና የምግብ ድጋፍ ፕሮግራም (DFAP) ፕሮጀክት ዳይሬክተር አቶ ጉቱቴሶ እንደገለፁት፤ የዘንድሮው ፕሮጀክት በዋናነት የሚያተኩረው የምግብ ዋስትናቸው ባልተረጋገጠ የኦሮሚያ የአማራና የደቡብ ክልል አካቢዎች ሲሆን ይህን ፕሮጀክት ለማሳካት የ3.8 ቢ. ብር በጀት ማግኘታቸውን ጠቅሰው፣ የአማራው ከሁለት ሳምንት በፊት ይፋ መሆኑንና የደቡቡ በቅርቡ በሀዋሳ እንደሚጀመር ተናግረዋል፡፡ የምግብ ዋስትናቸው ላልተረጋገጠ የሦስቱ ክልል አካባቢ ማህበረሰቦች ከምግብ ድጋፍ በተጨማሪ የተቀናጁ በርካታ ስራዎች ይከናወናሉ ያሉት አቶ ጉቱ ከነዚህም መካከል በግብርና፣በጤና፣ በአየር ንብረት ለውጥ፣ በንፁህ የመጠጥ ውሃ አቅርቦት በአኗኗር ዘይቤ በገጠር ስራ ፈጠራና በመሰል ስራዎች ላይ በማተኮር ድርቁን ተከትሎ የመጣውን የምግብ እጥረት እንዲቋቋሙ ይደረጋል ተብሏል፡፡