Administrator

Administrator

  ግብፅና ደቡብ አፍሪካ የአሸማጋይነት  ሚናን መርጠዋል፤ኢትዮጵያስ?

ባለፈው ቅዳሜ መስከረም 26 ቀን 2016 ዓ.ም በአሜሪካና አጋሮቿ የሽብርተኛ ድርጅት ተብሎ የተበየነው እስላማዊው የሃማስ ቡድን፣ በእስራኤል ላይ የፈፀመውን ድንገተኛ ጥቃት ተከትሎ፣ በተቀሰቀሰው የእስራኤል-ሃማስ ጦርነት ዙሪያ የአፍሪካ መንግስታት የተለያዩ አቋሞችን አንፀባርቀዋል - አንዱን ደግፈው ሌላውን  በማውገዝ፡፡

በእርግጥ የትኛውንም ሳይወግኑና ሳይቃወሙ ገለልተኛነታቸውን ለማንፀባረቅ የሞከሩም አልጠፋም-ናይጀሪያ ትጠቀሳለች፡፡ እስካሁን በእስራኤል-ሃማስ ጦርነት ገዳይ ትንፍሽ ያላሉ የአፍሪካ መንግስታትም አሉ፡፡

በሌላ በኩል፤ አቋም ሳይዙ የአሸማጋይነት ወይም የአስታራቂነት ሚናን የመረጡም አገራት ታይተዋል - ግብፅና ደቡብ አፍሪካ፡፡

የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን በበኩሉ፤ በሁለቱ ወገኖች መካከል ግጭት እንዲቆምና  ወደ ድርድር ጠረጴዛ እንዲመጡ  ጥሪ አስተላልፏል፡፡

የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር መለስ ዓለም፣ በእስራኤል- ፍልስጤም ጦርነት ጉዳይ የኢትዮጵያ አቋም ምን እንደሆነ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ "ኢትዮጵያ በእስራኤል- ፍልስጤም ጉዳይ ዙሪያ ከዚህ በፊት ካላት አቋም የተለየ አቋም አልያዘችም፣ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ህብረት አቋም የሆነው የሁለት ሉዓላዊ ሀገር መሆን ችግሩን ይፈተዋል የሚለው አቋም ትናንትም ሆነ ዛሬም ትክክል እንደሆነ ታምናለች" ብለዋል።

የኮንጎ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት ፌሊክስ ኬሲሽኬዲ፣ ከእስራኤል ጋር በአጋርነት እንደሚቆሙ ገልጸው፤አገራት ሽብርተኝነትን በሁሉም መልኩ ለመዋጋት አንድነትን መፍጠር እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡

የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ በተመሳሳይ፣ ከእስራኤል ጎን በአጋርነት እንደሚቆሙ በትዊተር ገጻቸው ባሰፈሩት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡

“ዓለማቀፉ ማህበረሰብ፤ የዚህን አስከፊ የሽብር ወንጀል ፈፃሚዎች፣ አደራጆች፣ የገንዘብ ድጋፍ አድራጊዎችና ደጋፊዎች  ተጠያቂ በማድረግ፣ በፍጥነት ለፍርድ ለማቅረብ መንቀሳቀስ አለበት፡፡” ብለዋል - ፕሬዚዳንት ሩቶ፡፡

 “ኬንያ ከቀረው ዓለም ጋር እስራኤልን በመደገፍ በአጋርነት ትቆማለች”፤ ያሉት ፕሬዚዳንቱ፤ “ሽብርተኝነትን እንዲሁም በአገሪቱ ውስጥ በንጹሃን ሲቪሎች ላይ የተፈጸመውን ጥቃት ሙሉ ለሙሉ  ታወግዛለች” ብለዋል፡፡

የኡጋንዳው ፕሬዚዳንት ዩዌሪ ሙሴቪኒ በበኩላቸው፤ “በእስራኤል - ፍልስጤም ዳግም አዲስ ግጭት መከሰቱ አሳዛኝ ነው፡፡ ለምንድን ነው ሁለቱ ወገኖች የሁለት ሉአላዊ አገራት መፍትሄን የማይተገብሩት? በተለይ ሊወገዝ የሚገባው፤ ተዋጊዎች ያልታጠቁ ሲቪሎችና ንጹሃንን ኢላማ ማድረጋቸው ነው፡፡” ብለዋል፡፡

የግጭት መባባስና የሰው ህይወት መጥፋት እንዳሳዘናቸው የገለፁት የጊኒ ቢሳው ፕሬዚዳንት ኡማሮ ሲሶኮ ኢምባሎ፤ በጋዛ ሰርጥ የተኩስ አቁም እንዲታወጅ  ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ኢምባሎ አክለውም፤ “ጊኒ ቢሳው ጦርነትን በቅጡ የምትረዳ ነገር ግን የሰላም አገር እንደመሆኗ፣ በጋዛ ሰርጥ ባለው ሁኔታ ከልብ ታዝናለች፡፡” ብለዋል፡፡

“በሚያሳዝን ሁኔታ በሃማስ የአየር ድብደባ ተፈፅሟል፤ እንዲያም ሆኖ ሁለቱም ወገኖች ግጭት እንዲያቆሙ እንጠይቃለን፤ ምክንያቱም የብዙዎች ህይወት እየጠፋ ነው” ሲሉ አፅንኦት ሰጥተው ተናግረዋል- ኢምባሎ፡፡

የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ሳይሪል ራማፎሳ፣ ከትላንት በስቲያ ሃሙስ፣ ከደቡብ አፍሪካ የግጭት አፈታት ልምድ በመውሰድ፣ የእስራኤል - ፍልስጤም ግጭን ለመሸምገል ዝግጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ራማፎሳ በተጨማሪም፣ እርዳታ በአስቸኳይ ለሚያስፈልጋቸው ወገኖች መድረስ ይችል ዘንድ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በፍጥነት “የሰብአዊ ኮሪደር” በመካከለኛው ምስራቅ እንዲከፈት ጠይቀዋል፡፡

የተለመደውን የአሸማጋይነት ሚናዋን የቀጠለችው ግብፅ፤ ሁለቱም ወገኖች ከግጭት “ራሳቸውን እንዲያቅቡ” ጥሪ ያቀረበች ሲሆን፤ “የግጭት መባባስ ስለሚያስከትለው ከፍተኛ አደጋ” አስጠንቅቃለች፡፡ የግብፅ ፕሬዚዳት አብደል ፋታህ አልሲሲና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትራቸው፣ ከአውሮፓ ህብረት የዲፕሎማሲ ሃላፊ ጆሴፕ ቦሬል እንዲሁም ከኢሜሬትስ፣ ዮርዳኖስ፣ ቱርክ፣ ፈረንሳይና ጀርመን ባለስልጣናት ጋር በጉዳዩ ዙሪያ መወያየታቸውን ተናግረዋል፡፡


የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሞሳፋኪ ማሃማት በበኩላቸው፤ ሁለቱም ወገኖች በአፋጣኝ ወታደራዊ ግጭትን አቁመው ወደ ድርድ እንዲመጡ ጥሪ አቅርበዋል - በመግለጫቸው፡፡

“የአፍሪካ ህብረት ሊቀመንበር ሁለቱም ወገኖች በአስቸኳይ ወታደራዊ ግጭትን አቁመው፣ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ፣ ወደ ድርድር ጠረጴዛ በመመለስ፣ የሁለት ጎን ለጎን የሚኖሩ ሉአላዊ አገራት መርህን እንዲተገብሩና የፍልስጤም ህዝብንና የእስራኤል ህዝብን ፍላጎቶች እንዲያስጠብቁ ጥሪ አቅርበዋል፡፡” ይላል - መግለጫው፡፡

“ሊቀመንበሩ በተጨማሪም፣ ዓለማቀፍ ማህበረሰቡ በተለይም ተፅዕኖ ፈጣሪ ሃያላን አገራት፤ ሰላም የማስፈንና የሁለቱን ህዝቦች መብቶች የማረጋገጥ ሃላፊነታቸውን ይወጡ ዘንድ ጠይቀዋል፡፡” በመግለጫው፡፡

 በእስራኤል-ሃማስ ጦርነት ላይ ገለልተኛ አቋም ያንፀባረቀችው ናይጀሪያ፤ “የግጭትና የአፀፋ ምላሽ አዙሪት”፤ ለሁለቱም ወገን ሰላማዊ ህዝቦች፣ “ማብቂያ የሌለው የስቃይ አዙሪት” ይፈጥራል ስትል አስጠንቅቃለች፡፡

በሌላ በኩል፣ የአልጀሪያ፣ ቱኒዝያ፣ ጅቡቲና ሞሮኮ መንግስታት ለፍልስጤም ሙሉ ድጋፋቸውንና አጋርነታቸውን ገልፀዋል -  እስራልን በመቃወምና በማውገዝ፡፡

በኡጋንዳ ካምፓላ የሰብአዊ መብት አንቂ የሆነው ኢብራሂም ሴንዳውላ፤ በእስራኤል - ሃማስ ጦርነት ለአንዱ ወይም ለሌላው መወገን ግጭትን ያባብሰዋል ሲል ለደቸቨሌ ተናግሯል፡፡

“የአውሮፓ መሪዎች የሰላም ጥሪ ከማቅረብ ይልቅ የእስራኤልን ጥቃት መደገፋቸው አስገራሚ ነው፤ በተመሳሳይ ሃማስ እስራኤል ላይ የፈፀመውን ጥቃት አንዳንድ ሰዎች ሲደግፉና ሲያደንቁ ማየት ያስገርማል፡፡ ይሄ አሳዛኝ ነው” ብሏል - ሴንዳውላ፡፡

* መገናኛ ብዙኃን ከችግር ፈጣሪነት ወጥተው ፖለቲካውን መምራት አለባቸው ተብሏል  

የኢትዮጵያ አርታኢያን ማህበር፤ "Media Polarization; How Editorial Policy Counteracts Polarization in the News Media" በሚል ርዕስ፣ በመገናኛ ብዙኃን ዋልታ-ረገጥነት ዙሪያ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ  ሳምንታዊ የቁርስ ላይ ውይይቱን አካሄደ።

የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የዲጂታል ሚዲያ ዋና አዘጋጅ አቶ ነብዩ ወንደሰን፣ በርዕሰ-ጉዳዩ ላይ ለውይይት መነሻ ሃሳብ የሚሆን ፅሁፍ አቅርበዋል።

አቶ ነብዩ በፅሁፋቸው፣ ቀደም ሲል የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን በሁለት ይከፈል እንደነበር (የመንግስትና የግል) አውስተው፤ አሁን ግን በአራት ነው የሚከፈለው ብለዋል። ሲዘረዝሩም፤ የመንግሥት፣ የግል፣ የኢትዮጵያን አንድነት የሚያቀነቅኑና ብሔርን መሰረት ያደረጉ መገናኛ ብዙኃን ናቸው ብለዋል፡፡  

የመገናኛ ብዙኃን ዋልታ-ረገጥነት፣ የተበላሸው ፖለቲካችን ነጸብራቅ መሆኑንም አስረግጠው ተናግረዋል፡፡

በአገሪቱ ለዘመናት የተከማቸ የፖለቲካ ችግር እንዳለ፣ አለመተማመንና ጥርጣሬ መስፈኑን  እንዲሁም በፖለቲካዊ ክርክራችን ከምክንያታዊነት ይልቅ ስሜታዊነት እንደሚንፀባረቅ ያነሱት ፅሁፍ አቅራቢው፤ መገናኛ ብዙኃኑም  ከዚህ  ውጭ መሆን ስለማይችሉ ዋልታ-ረገጥ ሆነዋል ብለዋል።

ዋልታ-ረገጥነት በሁሉም መገናኛ ብዙኃን ላይ የሚስተዋል ክስተት ቢሆንም፣ እንደ አሸን በፈሉት ብሔርን መሰረት ያደረጉ መገናኛ ብዙኃን ላይ የበለጠ  ጎልቶ እንደሚስተዋል የጠቀሱት አቶ ነብዩ፤ ጋዜጠኞች ገለልተኛ ሆነው እውነቱን በሚዛናዊነት ከመዘገብ ይልቅ ለመጡበት ብሔርና ሃይማኖት የሚወግኑ  እየሆኑ መጥተዋል ሲሉ ተችተዋል፡፡

የመገናኛ ብዙኃን ዋልታ-ረገጥነት በቅርቡ በቤተክህነት ውስጥ በተከሰተው ችግር በግልጽ ተንፀባርቋል ያሉት ፅሁፍ አቅራቢው፤ ከፊሎቹ ቤተክህነትን ወግነው ሲዘግቡ፣ የተቀሩት ደግሞ ተለይተው የወጡትን ቡድኖች በመወገን  መዘገባቸውን በምሳሌነት ጠቅሰዋል፡፡

መገናኛ ብዙኃን ገለልተኛ ሆነው እውነቱን ከመዘገብ ይልቅ ዋልታ-ረገጥ መሆናቸው ለጋዜጠኝነት ሙያ አደጋ ከመሆኑም ባሻገር  አገርን  ለግጭትና ብጥብጥ እየዳረገ እንደሚገኝም አቶ ነብዩ ተናግረዋል፡፡
 
 መገናኛ ብዙኃኑ የሚስተካከሉት የፖለቲካው ዋልታ-ረገጥነት ሲስተካከል ነው የሚል አቋም ያንጸባረቁት  አቶ ነብዩ፤ መገናኛ ብዙኃኑ የኤዲቶሪያል ነፃነታቸውን ጠብቀው እንዲሰሩ ጥረት ማድረግን፣ እንዲሁም ሃላፊነት የተመላበት ጋዜጠኝነትን ማጎልበትን እንደ መፍትሄ ሃሳብ ጠቁመዋል፡፡

የማህበሩ አባላትና ተጋባዥ እንግዶች በርዕሰ ጉዳዩ ላይ የተለያዩ  ሃሳቦችን ያንሸራሸሩ ሲሆን፤ የሚበዙት አስተያየት ሰጪዎች የሚዲያውን መልክአ-ምድር በመቀየር ረገድ አርታኢያን የጎላ ሚናና አስተዋፅኦ እንደሚኖራቸው አስምረውበታል፡፡

መገናኛ ብዙኃኑ የተበላሸው የፖለቲካችን ሁኔታ ነፀብራቅ መሆኑን የተቀበሉ አንድ አስተያየት ሰጪ፤ እንዲያም ሆኖ መገናኛ ብዙኃን የፖለቲካውን መልክአ-ምድር መቀየር የሚያስችል አጀንዳ መቅረፅ አለባቸው ብለዋል፤ ከችግር ፈጣሪነት ወጥተው  ፖለቲካውን መምራት እንዳለባቸውም  በማከል፡፡

አብዛኛው ሰው ለመገናኛ ብዙኃን ያለው ግምትና አመለካከት የተዛባ ነው ያሉት ሌላው የማህበሩ አባል፤ የመገናኛ ብዙኃንን ዋልታ-ረገጥነት ማስተካከል የምንችለው በመጀመሪያ በህብረተሰቡ ዘንድ ስለ መገናኛ ብዙኃን ትክክለኛ ግንዛቤ መፍጠር ስንችል  ነው ብለዋል፡፡

ፅሁፍ አቅራቢው፣ የመገናኛ ብዙኃን ዋልታ-ረገጥነት፣ የፖለቲካው ዋልታ-ረገጥነት ነጸብራቅ ነው በሚል ያቀረቡትን ሃሳብ ያልተቀበሉ አንድ አስተያየት ሰጪ፤ የመገናኛ ብዙኃን ዋልታ-ረገጥነት ዛሬ የተፈጠረ አይደለም ብለዋል፡፡ እርሳቸው እንደሚሉት፣ የመገናኛ ብዙኃን ዋልታ-ረገጥነት ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፖለቲካውን ዋልታ-ረገጥነት ተከትሎ የተፈጠረ ሳይሆን፤ ከደርግም ጀምሮ በኢህአዴግም ጭምር የተስተዋለ ክስተት ነው፡፡

ለመገናኛ ብዙኃን ዋልታ ረገጥ መሆን ተጠያቂ የሚያደርጉትም በተለያዩ ጊዜያት ሥልጣን ላይ የወጡ መንግሥታትን ነው፤ መንግሥታት የሥልጣን ዕድሜያቸውን ለማራዘም ሲሉ መገናኛ ብዙኃኑን የአንድ ወገን ፕሮፓጋንዳ ብቻ እንዲያስተጋቡ  ያደርጓቸዋል ሲሉ አስረድተዋል፡፡

የመገናኛ ብዙኃንን ዋልታ-ረገጥነት ለማስተካከልም መፍትሄው ያለው በመንግሥት እጅ መሆኑን የጠቆሙት አስተያየት ሰጪው፤ ጉዳዩ የመንግሥትን የፖለቲካ ቁርጠኝነት የሚጠይቅ ነው ብለዋል፡፡  

መንግሥትስ ምን እያለ  ይሆን??

Saturday, 07 October 2023 21:05

የ“ነገራ ነገር” ነገር

የደራሲ አብረሃም ዮሴፍ “ነገራ ነገር” የተሰኘ የግጥም መድበል ለንባብ በቃ፡፡
ጋዜጠኛና ደራሲ አንተነህ ይግዛው፣ ስለ ግጥም መድበሉ ያሰፈራት አጭር ማስታወሻ፣ መድበሉን ለመተዋወቅ ድልድይ ትሆናለች፡፡ እነሆ፡-
“ነገር እንደ ቁስል ሌት ተቀን ውስጥ ውስጡን የሚነዘንዛት፣ ሃሳብ እንደ ወንፊት ነጋ ጠባ ሳይል የሚወዘውዛት፣ የሆነች ባይተዋር ነገር የገባት ነፍስ በሃሳብ ስትባትል፣ የሆነ ጥግ ይዛ ካባዘተችው ቃል ባል አዘቦት ሳትል፣ የስሜት ልቃቂት ያሳብ ዘሃ ስንኝ የሐረጋት ፈትል ነው የተሸመነው - “ነገራ ነገር”፡፡
“ከገጣሚው ነፍስ የጎደለች አንዲት ሴት አለች፤ ከጎኑ የተነደለች አንዲት ሽንቁር፡፡ ገጣሚው በዚያች ሽንቁር በኩል አጮልቆ አለምን የሚያይባት፤ እውነትን፣ ህይወትን፣ እምነትን፣ ውበትን… መላ ጽንፈ አለሙን የሚያስስባት የሚታዘብባት፣ የሚፈክርባት፣ የሚዘክርባት የነፍስ ኪታቡ ናት - “ነገራ ነገር”፡፡
“በየነገራ ነገሩ መሃል ያቺ ሴት አለች፡፡ ሄዳለች ቢላትም በሄደበት ሁሉ የምትከተለው፤ ትታኛለች ቢልም ትታ የማትተወው፣ በሄደበት ሁሉ እየተከተለች የምትወዘውዘው፣ የምትጠዘጥዘው፣ የምትነዘንዘው ያቺ ቁስል አለች፡፡ ነገሩን ሲፈትሽ፣ ነገሩን ሲመዝን፣ ነገሩን ሲፈክር፣ ነገሩን ሲዘክር በእሷ በኩል ነው፡፡ የትም ብሎ ብሎ ዞሮ የሚያርፍባት፣ የትም የትም ቢበር ሰርክ የሚከንፍባት ዛፉም ክንፉም እሷ ናት፡፡
“ገጣሚው ጸጸትን ከተስፋ፣ ውዳሴን ከእርግማን፣ አብሮነትን ከመለየት፣ ፍቅርን ከጥላቻ፣ ሃዘንን ከደስታ እያሰናሰለ የሸመናት ጉራማይሌ ጥበብ ናት - “ነገራ ነገር”፡፡  
“ገጣሚው የቃላት ሃብታም ነው፡፡ የመነቸከውን የቀን ተቀን ነገር፣ ተራ እሚመስለውን የዕለት ከዕለት ጉዳይ፣ ሞልቶ ከተረፈው ሰፊ የቃል ሙዳይ ሁነኛ ቃል መርጦ በማልበስ የአዘቦቱን የክት አድርጎ ማቅረብ የተካነበት ነው፡፡ ቃል እያዳወረ ትዝታውን ያልማል፤ ተስፋውን ይዘክራል፡፡ ከተፈጥሮ ጋር ይጫወታል፤ ከሳር ከቅጠሉ፣ ከዝናብ ከጠሉ ጋር ይነጋገራል፡፡”

- የአውሮፓ ህብረት፣ የመርማሪ ቡድኑ የሥራ ጊዜ እንዲራዘም የሚያስችል  ረቂቅ ሃሳብ አለማቅረቡ ተኮንኗል
 በኢትዮጵያ የተፈጸሙ የመብት ጥሰቶችን እንዲመረምር   በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን  የተቋቋመው የባለሞያዎች ቡድን የምርመራ ጊዜ እንዲያራዝም  በበርካታ አለም አቀፍ የሰብአዊ መብት ድርጅቶች  በተደጋጋሚ ጥሪ ሲደረግ ቢቆይም፣ የመርማሪ ቡድኑ የስራ ጊዜ ሳይራዘም ቀርቷል።
የመርማሪ ቡድኑ የስራ ጊዜ ሳይራዘም የቀረው ከየትኛውም የአለም ክፍል ለመንግስታቱ ድርጅት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ ቡድኑ የቆይታ ጊዜውን  እንዲያራዝም የሚጠይቅ  ረቂቅ ሀሳብ ባለመቅረቡ  መሆኑ ታውቋል።
የዓለማቀፉ የኢትዮጵያ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች መርማሪ ኮሚሽን የጊዜ ቆይታን ለማራዘም ረቂቅ የውሳኔ ሃሳብ ለተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት የማቅረቢያው ቀነ ገደብ ከትናንት በስቲያ ተጠናቋል።  ለኮሚሽኑ መቋቋም ቁልፍ ሚና የተጫወተው አውሮፓ ኅብረት፣ የኮሚሽኑን ቆይታ ለማራዘም የሚያስችል የውሳኔ ሃሳብ እንዲያቀርብ ተደጋጋሚ ጥያቄ ቢቀርብለትም ሣያቀርብ ቀርቷል ።  
የሂዩማን ራይትስ ዎች የአውሮፓ ዳይሬክተር ፊሊፕ ደም፣ የአውሮፓ ህብረት፣  የመርማሪ ቡድኑ የስራ ጊዜ እንዲራዘም ረቂቅ ሃሳብ አለማቅረቡን አጥብቀው ኮንነዋል፡፡
የመርማሪ ቡድኑ እንዲቋቋም የውሳኔ ሃሳብ አቅርቦ ያጸደቀው አውሮፓ ኅብረት ረቂቅ የውሳኔ ሃሳብ እንዲያቀርብ ሂዩማን ራይትስ ዎችን ጨምሮ በርካታ ተቋማት ተደጋጋሚ ጥሪ ሲያቀርቡለት  ቆይተዋል ።   ሂዩማን ራይትስ ዎች፣  የአውሮፓ ህብረት  የቡድኑ የምርመራ ጊዜን እንዲያራዝም  በማድረጉ ረገድ  ከፍተኛ ሚና እንደሚጠበቅበትም አመልክቷል ።
ተበዳዮችም ሆኑ የሰብአዊ መብት ተቆርቋሪ ድርጅቶች፣ የሀገሪቱ  የፍትህ ተቋማት ፍትህ ያሰፍናሉ የሚል እምነት እንደሌላቸው የሚገልፀው  አለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ተቋም፤  አለም አቀፉ የመርማሪዎች ቡድን እንዲቋቋም ከፍተኛ ሚና የተጫወተው የአውሮፓ ህብረት አሁንም የስራ ግዜው እንዲራዘም ረቂቅ ሃሳብ በማዘጋጀት ረገድ የመሪነት ሚና እንዲጫወት ሲወተውት ሰንብቷል።  
በዓለማችን ከፍተኛ ተጽዕኖ ፈጣሪ የሆኑ ታላላቅ የሰብአዊ መብት  ጥሰቶች ተሟጋች ድርጅቶች በጋራ በመሆን የመንግስታቱ ድርጅት፣ በኢትዮጵያ የሚያካሂደውን የሰብአዊ መብት ጥሰት  እንዲመረምር  ያቋቋመው ቡድን ተልዕኮውን ለተጨማሪ አንድ አመት እንዲያራዝም  መጠየቃቸው የሚታወስ ሲሆን ጥያቄውን ያቀረቡት አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ ኦክ፤ስፋም እና የአለም የሰላም ፋውንዴሽንን ጨምሮ 63 የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅቶች በጋራ በጻፉት ደብዳቤ ነበር ።
የአለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ኤክስፐርቶች በኢትዮጵያ (ICHREE) ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤት ባቀረበው ሪፖርት በኢትዮጵያ አሁንም የጦር ወንጀልና በሰብአዊነት ላይ የሚፈጸም ወንጀል እንደቀጠሉ መሆናቸውን አመልክቷል።















Saturday, 07 October 2023 20:40

“ይቅርታ”

(የአጭር አጭር ልብወለድ)

ፊልም ለማየት ከባለቤቴ ጋር የገባሁ ዕለት ነበር ይህን ስህተት የፈጸምኩት፡፡ ወገግ የማይለው አታካቹ ፊልም የሲኒማ ቤቱን ከላይ እታች ድረስ አጨላልሞታል፡፡ በዚህ ላይ ፊልሙ የማያስደስት ነበር፡፡ ድብርታም የሚሉት ዓይነት፡፡
ከሩቅ ባትሪውን በራ ጠፋ እያደረገ አይስክሬም የሚሸጠውን ሰውዬ ሳይ፣ ለእኔና ለዱቪ አይስክሬም ለመግዛት አሰብኩና ተነስቼ ሄድኩኝ፡፡ ስመለስ ድርሻውን ለባለቤቴ ስሰጠው እጄን አጥብቆ ያዘኝ፡፡
“እወድሃለሁ ፍቅሬ” አልኩና በጆሮው ሹክ አልኩት፡፡ በአይስክሬም በታጨቀው አፉ እየተንተባተበ፣ እሱም እንደሚያፈቅረኝ ነገረኝ፡፡
“እዚህ ተቀምጬ ይህን ቀፋፊ ፊልም ከማየት ይልቅ ከአንተ ጋር ቤት ብንሆን እንዴት ደስ ባለኝ---” ስለው እጆቹን በአንገቴ ዙሪያ አደረገና አቀፈኝ፡፡
አንዲት ሴት መተላለፊያ መንገዱን በእግሮቼ ስለዘጋሁባትና ማለፍ ስላልቻለች ነው መሰለኝ፤ “ይቅርታ --” አለችኝ “እህት ይቅርታሽንና-”  የጀመረችውን ንግግሯን ሳትቋጨው እንድታልፍ ብዬ እግሮቼን ሰብሰብ አደረግሁ፡፡ ነገር ግን ካለችበት ቦታ ነቅነቅ ሳትል አሁንም ዳግም “ይቅርታሽን” ማለቱን መረጠች፡፡ የአሁኑ አነጋገሯ  ግን ጠብ ያለሽ በዳቦ ይመስላል፡፡
ለሦስተኛ ጊዜ “እህት ይቅርታሽንና የተቀመጥሽው በመቀመጫዬ ላይ ነው” አለችና ጮኸች፡፡
ሴትዬዋ ተናግራ ስታበቃና ፊልሙ ሲጨርስ አንድ ሆነ፡፡
ወዲያው መብራቱ በራና ሁለት ወንበር መደዳዎች ከፊት ለፊቴ ሳይ፣ በጭንቀት “የት ቀረች” ብሎ አንገቱን አስሬ የሚያዞረውን የእኔውኑ ባለቤት ዱቪን አየሁት፡፡
ምንም እንኳን ስህተቱን የሰራሁት እኔ ብሆንም፣ አሁንም ቢሆን “ይቅርታ” ብላ የጮኸችብኝ ሴትዮ፣ ለባሏ የሰጠሁትን የአይስክሬም ዋጋ መክፈል አለባት እላለሁ፡፡
ደራሲ፡- ባርባራ ዬቪስ
ትርጉም፡- አስፋው ደገፉ

እንቁራሪቶች ጦጣዎች፣ አይጦችና የዱር አራዊቱ ንጉስ አንበሳ የሚኖሩበት ትልቅ ደን አለ፡፡
እንቁራሪቶቹ ከደኑ አጠገብ ካለው ኩሬ ውስጥ ነው የሚኖሩት፡፡ አንበሳ የሚጠይቃቸውን ሁሉንም ለመታዘዝ ነው ሌሎቹ የሚኖሩት፡፡ አንድ ቀን እንቁራሪቶቹ፣ ጦጣዎቹና አይጦቹ በአንድነት መስክ ላይ በየበኩላቸው እየለቃቀሙ ሳሉ፤ አዳኞች አንበሳውን ሲያሳድዱት ተመለከቱ፡፡ እንቁራሪቶቹም፤ “ለጌታም ጌታ አለው! ሰው እኮ የአንበሳ ጠላት ነው አይለቀውም፡፡ ከዚህ መአት ለማምለጥ በሉ ወደ ኩሬአችን እንሂድ” አሉና ወደ ኩሬአቸው አመሩ፡፡ አይጦቹም፤ የደኑ ገዢ አንበሳ ነው ብለው ስለሚያስቡ “ሰዎችና አንበሶች አጥፊና ጠፊ ናቸው፡፡ የዚህ አንበሳ ጣጣ ለእኛም እንዳይተርፈን በጊዜ ወደ ጎሬአችን  ገብተን እንሽሽ” አሉና ሄዱ፡፡ ጦጣዎቹ፤ “ሰው አንበሳን ሲጠላ እንደ ጉድ ነው፡፡ በጊዜ ዛፋችን ላይ እንውጣ” ብለው በየዛፎቻቸው ላይ ተንጠላጥለው ወጡ፡፡
አዳኞቹ አንበሳውን ገድለው ቆዳውን ገፈው ወሰዱ፡፡ አዳኞቹ ከሄዱ በኋላ እንቁራሪቶቹ፣ ጦጣዎቹና አይጦቹ እንደገና ተሰባስበው፤ ጦጣ ስለ ዛፍ ላይ ኑሮ፣ እንቁራሪት ስለ ኩሬ ኑሮ፣ አይጥ ስለ ከመሬት በታች ኑሮ አወጉና የአንበሳውን አሟሟት እያነሱ በየበኩላቸው የሚያስተዳድሩት ግዛት እንዳላቸው በመጥቀስ ወጋቸውን ሲሰልቁ ቆዩ፡፡
በነጋታው በኩሬ ውስጥ ያሉትን ነብሳት ሁሉ ለመብላት የሚፈልጉ አጥማጆች ሲመጡ ጦጣዎች ወደ ዛፋቸው፣ አይጦች ወደ ጉድጓዳቸው ሮጡ፡፡ እንቁራሪቶች ግን ሁሉም ከኩሬው ተለቃቅመው ተወሰዱ፡፡ ጦጣዎችና አይጦች እንደ ልማዳቸው በሦስተኛው ቀን ተገናኝተው እያወጉ፤ “እንቁራሪቶቹን ምን አድርገዋቸው ይሆን?” እያሉ ተጠያየቁ፡፡  “ሰው እኮ ጨካኝ ነው፡፡ በልተዋቸው ይሆናል” አሉ ጦጣዎቹ፡፡ “ምናልባት እስኪበሏቸው በእንክብካቤ ያኖሯቸው ይሆናል” አሉ አይጦቹ፡፡
ይህንኑ እያወጉ ሳሉ የአይጥ ወጥመድ የያዙ በርካታ ሰዎች መምጣታቸውን አዩ፡፡ ጦጣዎቹ ፈጥነው ወደ ዛፋቸው ወጡ፡፡ አይጦቹ ወደ ጉድጓዳቸው ሮጡ፡፡ ባለ ወጥመዶቹ አድፍጠው ወጥመዶቻቸውን በጥንቃቄ በየጉድጓዳቸው አፋፍና ውስጥ አኖሩባቸው፡፡
በነጋታው አይጦች የወጥመዶቹ ሲሳይ ሆኑ፡፡ ጦጣዎቹም፤ “አንበሳው ሰው ጠላቱ መሆኑን እረስቶ ጉልበቱን ተማምኖ በደን ውስጥ ሲንጎማለል ተበላ፡፡ እንቁራሪቶቹም ማምለጫ በሌለው ኩሬ ውስጥ እንደተወሸቁ መውጫ ሳያበጁ ቀለጡ፡፡ እነዚህ አይጦችም ገብተው ከማይወጡበት ጉድጓድ ውስጥ ተቀርቅረው ብቅ ሲሉ በወጥመድ እየታነቁ ሲጥ አሉ፡፡ እኛ ግን ዛፍ ላይ ነንና  ሰው ወደ እኛ ሲመጣ በቀላሉ ስለሚታየን፣ ከዛፍ ዛፍ እየዘለልን ደብዛችንን እናጠፋበታለን” ተባባሉ፡፡
ጥቂት ቀናት ሰነባብቶ ሰዎቹ ወደ ጫካው መጡ፡፡ ጦጣዎቹም ማንም አይነካን ብለው ዛፋቸው ላይ እንዳሉ ቆዩ፡፡ የሰው ልጅ ጥፋት ሰለባ መሆናቸውን ያወቁት ግን ከዳር ዳር ደኑ በእሳት  መያያዙን ያዩ ጊዜ ነበር፡፡ ዛፍ ላይ ያሉት እዚያው እንደተንጠለጠሉ ተቃጠሉ፡፡ የወረዱትም በሰዎቹ አለቁ፡፡  የሚገርመው ግን አዳኞቹ ሰዎች ቤታቸው ሲደርሱ ቤታቸው በጠላቶቻቸው ተቃጥሎ ዶግ አመድ ሆኗል!
***
አለም የአጥፊና ጠፊ መድረክ ናት፡፡ ነግ በኔ ብሎ ገና በጠዋት ያልተጠነቀቀ፣ እጣ-ፈንታው እንደ ቀዳሚዎቹ ሟቾች ነው፡፡ የፋሲካ በግ፣ በገናው በግ እንደሳቀ መሞቱ ከአመት አመት የምናየው ሀቅ ነው፡፡ እኔ የራሴን ታሪክ እሰራለሁን እንጂ ሌሎች እኔን መሰሎች በታሪኩ ውስጥ ምን ጽዋ ደረሳቸው? ብሎ አለመጠየቅ፣ ምላሹን ካገኙም፣ የኔንስ ክፉ እጣ እንዴት እመክተዋለሁ ብሎ አለማውጠንጠን የአለምንም የሀገራችንንም የፖለቲካ ድርጅቶች፣ ቡድኖች፣ መሪዎችና ታዋቂ ግለሰቦች ታሪካዊ እጣ-ፈንታ ሳይታለም የተፈታ እንዲሆን ካደረገው ውሎ አድሯል፡፡ ነግ-በኔ አለማለት ክፉ እርግማን ነው፡፡
ለማርቲን ኒየሞይለር መታሰቢያ የተደረገው ፅሁፍ ይሄንኑ ይነግረናል፡፡ ማርቲን ኒየሞይለር (1892-1984) የፕሮቴስታንት ክርስቲያን የነበረ ጀርመናዊ ቄስ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ናዚዎችን በመቃወም ከባድ ዘመቻ በማካሄዱ እ.ኤ.አ ከ1938 እስከ 1945 ዓ.ም ለስምንት አመታት ማጎሪያ ካምፕ ውስጥ አስገብተው ሲያሰቃዩት ከርሞ ኋላ ተፈትቶ፣ ከ1961 እስከ 1968 ዓ.ም ለሰባት አመታት የአለም አብያተ-ክርስቲያናት መማክርት ፕሬዚዳንት ሆኖ የመራ ጠንካራ ሰው ነበር፡፡ ለሱ መታሰቢያ የተደረገው ጽሁፍ እነሆ፡-
የጀርመን ናዚዎች መጥተው በመጀመሪያ ያጠቁት ኮሙኒስቶችን ነበር፡፡ የኮሙኒስቶቹን በር እያንኳኩ ሲጨፈጭፏቸው እያየሁ እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም ኮሙኒስት አልነበርኩም፡፡
ቀጥለው አይሁዶቹንም ወረዱባቸው፡፡ የአይሁዶቹን በር ሲያንኳኩም እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም እኔ አይሁድ አይደለሁም፡፡
ከዚያ ወደ ሠራተኛ ማህበራቱ ዞሩ፡፡ የሠራተኞቹን በር ሲያንኳኩም እኔ ጭጭ አልኩ፡፡ ምክንያቱም የሠራተኛ ማህበሩ አባል ስላልነበርኩ አይመለከተኝም፡፡
ቀጥለው ካቶሊኮቹን ይፈጁ ጀመር፡፡ የካቶሊኮቹንም በር ሲያንኳኩ አሁንም እኔ ዝም አልኩ፡፡ ምክንያቱም እኔ ፕሮቴስታንት ስለሆንኩ አይመለከተኝም፡፡
በመጨረሻ የእኔን በር አንኳኩ፡፡ በዚያን ሰአት ግን ተነስቶ ሊናገር የሚችል ምንም ሰው አልተረፈም ነበር፡፡
(ለማርቲን ኒየሞይለር [ፍሬድሪሽ ጁስታቭ ኤሚል] መታሰቢያ የተፃፈ- 1949)
የፈለገው መንግስት፣ ይመቸኛል ባለው መንገድ ያሻውን ሀገር ሲረግጥ፣ ያሻውን መሳሪያ ሲጠቀም፣ በእኔስ ላይ ፊቱን ያዞረ እለት ምን ይውጠኛል?  የእኔስ በር የተንኳኳ እለት ማን አብሮኝ ይቆማል? ብሎ አለመጠየቅ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ዛሬ በየቻናሉ በቀጥታ ስርጭት በቴሌቪዥን የምናየው ጦርነት፣ እንደተዋጣለት የሲኒማ አልያም የትያትር ዝግጅት የውሸት እልቂት እስኪመስል ድረስ ያስገርማል፡፡ በአለም ታሪክ የመጀመሪያው ሳይሆንም አይቀር፡፡ የጋዜጠኞቹም ድምፀት “ጦርነቱ ሊጀምር ነው፤ አብረን እንከታተል” እንደማለት ሆኗል- የሰው ልጅ ሞት ምፀት! እንደ ትላንት ወዲያ “ኢምፔሪያሊዝም ውርደት ቀለቡ ነው”… የሚባልበት የቀዝቃዛው ጦርነት ዘመን አልፎ፤ እፎይ ብሎ አለም ለመተንፈስ አለመቻሉ ከመደገም የማይቀሩ ብዙ የታሪክ ስላቆች መኖራቸውን ያስገነዝበናል፡፡ እግረ-መንገዱንም ሃያላን መቼም በቃኝን እንደማያውቁ ዳግም ያስታውሰናል፡፡ የወታደራዊ ሃይል ግሎባላይዜሽን የት እንደሚደርስም ይጠቁመን ይሆናል፡፡ “ወተት ሰርቆ ከመጠጣት ይልቅ አፍ አለመጥረጉ ያሳፍረዋል” እንዲሉ፣ ትላልቁን የሃያላኑን ጥፋት ትቶ በእንጭፍጫፊ ላይ ማተኮር፣ ሌላ ጥፋት እንደመፈፀም መሆኑን ሳያስገነዝበን አያልፍም፡፡ ትንሹን አንባገነን ትልቁ አንባገነን፣ ሚጢጢውን ጉልበተኛ ግዙፉ ጉልበተኛ ሊውጠው ይመኛል፡፡ ይንጠራራል፡፡ ይስፋፋል፡፡ እስከዚያው እንቅልፍ የለውም፡፡ ህዝቡና አገሩ ከመጤፍ አለመቆጠሩ ግን የየዘመኑ ትራጀዲ ነው፡፡ የዛሬም፡፡ የታዋቂው ገጣሚ መንግስቱ ለማ፤ “ባንተ አልተጀመረም ያዳሜ ምኞት” “ከተጠቃው ‘መራቅ' አጥቂን ‘መጠጋት' የሚለውን ስንኝ እንደ መርህ የያዘው በርካታ መሆኑ ደግሞ መራር ትራጀዲ ያደርገዋል፡፡ “ጠባይ ያለው ልጅ ኑክሊየር ይሰጠዋል፡፡ ጠባይ የሌለው ልጅ የአሻንጉሊት ሽጉጥንም ይነጠቃል” አይነት ሆኗል፤ የሃያላኑ የአባትነት ባህሪ፡፡ ጉዳዩ ግን  የእኔን በር እስካላንኳኳ ድረስ “ለእኔ አገር አማን ነው” ብሎ ማሰብን መተውን ይጠይቃል፡፡ ሃያላን አልጠግብ ማለታቸው የስር የመሰረት ነውና፡፡
የሃያላኑን ተወት አድርገን አገራችን ስንገባም ነግ-በኔ ቁልፍ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ሌላ አገር ሲጠቃ ምን ግዴ ማለት፣ ሌላ ፓርቲ ሲገፋ ምን ቁቤ ማለት፣ ሌላ ሰው ሜዳ ሲወድቅ እንደ ፍጥርጥሩ ማለት፣ ቀን የጨለመ እለት ክፉ ነገር ነው፡፡ ትላንት በራሳችን መጥነንና ለክተን ያሰፋነውን የድንጋጌና የመርህ መጎናፀፊያ፤ ዛሬ ዳር እስከዳር አገሬውን ካላለበሰነው ብለን የምንታገልበት ሁኔታ የኋሊት ጉዞ ይመስላል፡፡ “ትንሽ ስንቅ የያዘ አስቀድሞ ይፈታል” እንዲሉ፤ አገርን የሚያህል ሰፊ ባህር የትንጧን ህልማችንን መፍቻ ለማድረግና አንዲቷን ቀጭን ኩታችንን ለልጁም ላዋቂውም አለብሰዋለሁ ብሎ፣ አይሆኑም ሲባሉ ግትር ማለት ደግ አይደለም፡፡ ቢያንስ የዋህነት፣ ሲበዛ በሰፊው ተወጥሮ መሰነጣጠቅ ነው ውጤቱ፡፡
“ከቆየን አንድ አመት፣ ከበላን የተከለከለ ሣር!” እንዳለችው ላም በድርጅታዊ አሰራርና ወገናዊነት፣ በዘመዳምነት፣ በእከክልኝ-ልከክልህ፣ “በአራዳነት” በወደቀው ዛፍ ምሳር በማብዛት፣ በእቁብም በእቁባትም በመመነዛዘር ለጊዜው ሙስናን ቢያስፋፉ፣ የስር የመሰረት ብቅ በሚልበት ሰአት ምነው አፌን በቆረጠው፣ ምነው እግሬን በሰበረው ማለትን አልያም “እኔ ከሞትኩን” መድገምን ያስከትላል፡፡ የተሰራንበትን ንጥረ ነገር በምንም አይነት ካባ ብንሸፍነው የማታ የማታ ብቅ ማለቱ ከቶ አይቀርም፡፡ “በትንባሆ የተገዛ ጦር፣ እገበያ መሃል ቢወረውሩት፣ ጓያ ጫፍ ላይ ይቆማል” የሚለው የወላይታ ተረትም የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡  


Saturday, 23 September 2023 21:20

“አያልቅበት” – ኤፍሬም!!

ጋዜጠኛ፣ ተርጓሚና ደራሲ ነው – ኤፍሬም እንዳለ። አለቀ። ከዚህ ውጪ ስለ እሱ ግላዊ ሕይወትና ማንነት፣ ጥረትና ልፋት በሕትመትና ብሮድካስት ሚዲያዎች ሲነገር ሰምቼ አላውቅም። የእሱም ፍላጎትም፣ ግድም አይመስለኝም፤ አደባባይ መውጣቱ። ደም ለመመለስ ቤቱን አቃጥሎ የሸፈተ ሰው፣ መልኩን አይደለም ጥላውን ሳያሳይ ጫካና ጥሻን ተከልሎ ወደ ዒላማው ጥይቱን እንደሚልከው ሁሉ፣ እሱም ካለበት ጥጋት ተሰትሮ በብዕር ከመተኮስ ውጪ በታይታ ሰውነቱ አይታወቅም።
ኤፍሬም ወደ ሰላሳ ለሚጠጉ ዓመታት – በእኔ ዕውቀት ከ”ፀደይ” መጽሔት ጀምሮ በተለያዩ ጋዜጦችና መጽሔቶች ላይ ምፀት - ለበስ ወጎችንና ጨዋታዎችን ሲያስኮመኩመን አሁን ድረስ አለ። ዘወትር ቅዳሜ ላለፉት አስራ ሰባት ዓመታት “ጨዋታዎቹን” የሚያስነብብባትን “አዲስ አድማስ” ጋዜጣን ባገላበጥኩና ጽሑፎቹን ባነበብኩ ቁጥር እጅጉን የምደመምበት ነገር ቢኖር የጨዋታዎቹ ለዛቸውን ጠብቀው መቆየታቸው፣ ዕይታዎቹና የሚያነሳቸው ጉዳዮች፣ እንዲሁም የብዕሩ ከዘመን ዘመን ሳትከሽፍ የኅብረተሰባችንን ጉዳዮች በራሱ በኅብረተሰቡ ወቅታዊው አስተሳሰብና አነጋገር እነሆ ማለቱ ነው። ትናንት አራዳ፣ ዛሬም አራዳ ነገም አራዳ እንደሆነ ስለመዝለቁ ያሳብቃሉ – ለወጉ ማዋዣነት ጣል የሚያደርጋቸው አስቂኝ ቀልዶችና ገጠመኞች።
ኤፍሬም፤ በ”ፀደይ” መጽሔት “እንጨዋወት አምድ”፣ “Ethiopian Herald” ጋዜጣ “Between you and me” አምድ ላይ በአምደኝነት  በ”The Sun” ጋዜጣ  ከአንጋፋ ጋዜጠኛ ያዕቆብ ወልደማርያም ጋር በአዘጋጅነት፣ በ”ምዕራፍ” ጋዜጣ ከእነ ስብሐት ገብረእግዚአብሄር ጋር በመሆን በዋና አዘጋጅነት፣ ካለፉት 17 ዓመታት ጀምሮ እስካሁን ደግሞ  በ”አዲስ አድማስ” ጋዜጣ ላይ አምደኛ ነው።
መጻሕፍትን ለንባብ በማብቃቱም ረገድ፤ እጅግ ተነባቢና ተወዳጅ የነበረውን የሮበርት ሉድለምን መጽሐፍ “ፍንጭ” በሚል ርዕስ ለንባብ አብቅቷል። የቱርካዊውን አዚዝ ኔሲን “እራሴን አጠፋሁ” የተሰኘ መጽሐፍም በኤፍሬም እንዳለ ተተርጉሞ ለህትመት የበቃ ነው። እሱ ያዘጋጀውን “ቤርሙዳ ትርያንግል”  የተባለ መጽሐፍም ከብዙ ዓመታት በፊት ማንበቤም ትዝ ይለኛል። “የዘመን ዱካ” እና “ሕይወት በክር ጫፍ”  የተሰኙ ሥራዎችም አሉት። በተለያዩ መጽሔቶችና “እፍታ” መጽሐፍ ላይ የወጡ የራሱንና ትርጉም አጫጭር ልቦለዶችን ለአንባቢያን አበርክቷል። “የጉራ ሊቅ”ን ያስታውሷል። “እንግሊዘኛን በቀላሉ” የተባለች ለእንግሊዘኛ መማሪያነት የምታገለግል በኪስ የምትያዝ ታዋቂ መጽሐፍም ነበረችው።  ጋዜጣና መጽሔት ላይ ወጥተው የተነበቡ ሥራዎቹንም በመጽሐፍ መልክ አሳትሟቸዋል።
በኢትዮዽያ ሬድዮ “ቅዳሜ  መዝናኛ” እና በሸገር ሬድዮ “የጨዋታ” ፕሮግራም ላይ የተላለፉ ተከታታይ እና አጫጭር አዝናኝ ድራማዎችን በመድረስና በመተርጎም ለአድማጮች እንዲደርሱ አድርጓል። ተደንቆበታልም።  “ስካይ ፕሮሞሽን” የሚል የማስታወቂያ ድርጅት አቋቁሞ እንቅስቃሴ ያደርግ እንደ ነበር አስታውሳለሁ – አሁን ይቀጥልበት አይቀጥልበት ባላውቅም።
አንዲት ሚጢጢ መጽሐፍ አበርክቶ ሰማይ ልንካ የሚል ውርንጫ ጸሐፊ በሞላበት ሀገር፣ ይህን ለሦስት አስርት ዓመታት ያህል ድምፁን አጥፍቶ ትልቅ ተግባር የከወነን ሰው አለማንሳት፣ አለማውሳት ትልቅ ሀፍረት ነው – ለሁሉም። ክብር ለሚገባው ሁሉ ክብር ይሁን፤ አበቃሁ!!!
ማሳሰቢያ:– ከኤፍሬም እንዳለ ሰብዕና፣ ሥራዎችና ጥረት አንፃር ይህ ልጥፍ ጽሑፍ 1% ያህል አይሰጠውም ከመቶው። ይሁን እንጂ ከእኔ በተሻለ ስለ እሱና ስራዎቹ የምታውቁ፣ በዚህች ቅንጭብ ጽሑፍ ላይ የታያችሁን ስህተት በእርማት፣ የቀረውን ደግሞ በአስተያየት ታሟሉታላችሁ ብዬ በማመን ነው እዚህ ያሰፈርኩት። ተሳትፎአችሁ ይጠበቃል!!!

አንድ የአርሜኒያ አፈ-ታሪክ እንዲህ ይላል፡፡
ከእለታት አንድ ቀን አንድ የአርሜኒያ ንጉስ፣ አፍ-ጠባቂዎቹን በመላ ሀገሪቱ ልኮ “ከድፍን አርሜኒያ በመዋሸት አንደኛ ለሆነ ሰው፣ ንጉሱ ከወርቅ የተሰራ ትልቅ ፍሬ ሊሸልሙ ይፈልጋሉ!” እያሉ እንዲነግሩና እችላለሁ የሚል ማንኛውም ሰው እንዲመጣ እንዲደረግ ትእዛዝ ይሰጣሉ። የሀገሩ ውሸታም ሁሉ ወደ ቤተ-መንግስት መጉረፍ ይጀምራል፡፡ ግቢውን መግቢያ መውጫ አሳጣው ሰዉ፡፡ እንደእየ ማእረጉ ከየኑሮ እርከኑ ያለ ሰው መጣ፡፡ መሳፍንትና ልኡላን፣ ታላቅ ነጋዴዎች፣ ገበሬዎች፣ ቀሳውስት፣ ባለፀጎችና ደሆች፣ ወፍራም ቀጭን፣ አጭር እረጅም፣ ቆንጆና አስቀያሚ፡፡ በአገሩ የቀረ የሰው አይነት ያለ አይመስልም፡፡
አርሜኒያ የውሸታም እጥረት ኖሮባት አያውቅም፡፡ ሁሉ እየመጣ ለንጉሱ ውሸቱን አወራ፡፡ ወሸከተ፡፡ ንጉሱ ግን ከዚህ ቀደም የውሸት አይነት በገፍ ሰምተው ስለነበር፣ አሁን እየሰሙአቸው ያሉት ውሸቶች እንደ ድሮ ውሸት አልጥምም አላቸው፡፡ ምርጥ የሚሉት ውሸት አጡ፡፡ ማዳመጡም ደከማቸው፡፡ በጣም ከመሰልቸታቸው የተነሳ ውድድሩን ያለአሸናፊ ሊዘጉት ፈለጉ-በጨረታው አልገደድም ብለው፡፡
ሆኖም በመጨረሻ አንድ ጭርንቁሳም ደሃ መጣ፡፡
“እህስ ምን ልርዳህ አንተ ዜጋ?” ሲሉ ጠየቁ ንጉሱ፡፡
“ንጉስ ሆይ” አለ ዜጋው ትንሽ እንደመደናገጥ ብሎ “እንደሚያስታውሱት ከዚህ ቀደም፤ አንድ እንስራ ወርቅ ሊሰጡኝ ቃል ገብተውልኝ ነበር” አላቸው፡፡
“ማ? እኔ? ለአንተ?”
“አዎን ንጉስ ሆይ፤ ለአያሌ ሰው ብዙ ቃል ስለሚገቡ እረስተውት ይሆናል እንጂ፤ በእርግጥ እሰጥሃለሁ ብለውኝ ነበር!”
“ይሄ ፍፁም ውሸት ነው! አንተ  ቀጣፊ ሰው ነህ! ምንም ገንዘብ ላንተ ልሰጥ ቃል አልገባሁም”
“እንግዲያው ይሄ ፍፁም ውሸት ነው ካሉ፤ ከወርቅ የተሰራ ትልቅ ፍሬ እሸልማለሁ ብለው አውጀው ነውና የመጣሁት፤ ሽልማቱ ለኔ ይገባኛል፡፡ የወርቁን ፍሬ ይስጡኝ” አላቸው፡፡
ንጉሱ ይሄ ዜጋ በዘዴ ሊያታልላቸው መሆኑን አሰቡና፤
“የለም የለም፤ አንተ ውሸታም አይደለህም” አሉት፡፡
“እንግዲያው ቃል የገቡልኝን አንድ እንስራ ሙሉ ወርቅ ይስጡኝ” አለ፤ ፍርጥም ብሎ፡፡
ንጉሱ አጣብቂኝ ውስጥ ገቡ፡፡ ከወርቅ የተሰራውን ትልቅ ፍሬ የግዳቸውን ለደሃው ሸለሙት፡፡
***
እውነተኛ ውሸት የሚዋጣለት ሰው እንኳ እንዳይጠፋ መመኘት ጥሩ ነው፡፡ ያ ሁሉ መኳንንት መሳፍንት፣ ነጋዴ ወዘተ ወሽክቶ ወሽክቶ የሚታመንና ማራኪ ውሸት መጥፋቱ ትልቅ ድክመት ነው፡፡ በአንፃሩ በገዛ አዋጁ፣ በገዛ መመሪያው፣ በገዛ ፕሮግራሙ፣ በገዛ እቅዱ አጣብቂኝ ውስጥ የሚገባ መሪ፣ አለቃ፣ ሃላፊ፣ የፖለቲካ ሰው፣ የፓርቲና የማህበር የበላይ ሃላፊ ሁሉ፤ ውሎ አድሮ የሚከፍለው እዳ እንዳለ ማስተዋል ደግ  ነው፡፡ የምንገባው ቃል እራሳችንን መልሶ የሚጠልፈን እናም የሚጥለን ሊሆን እንደሚችል አለመዘንጋት ነው፡፡
በታሪክ “አደገኛው ኢቫን” (Ivan the Terrible) በመባል ይታወቅ የነበረው የሩሲያ ንጉስ፤ አንዴ አስከፊ አጣብቂኝ ውስጥ ወድቆ ነበር ይባላል፡፡ ይሄውም፤ በአንድ በኩል፤ ሀገሪቱ  ለውጥና መሻሻል ትፈልጋለች፡፡ በሌላ በኩል፣ ወደፊት ገፍቶ ወደተሻለ አገር እንዳይለውጣት አቅም አጣ፡፡ በዙሪያው ያሉት ሁነኛ የሚላቸው ሰዎች ደግሞ ገበሬውን  ሡሪ-ባንገት-አውልቅ የሚሉት ልኡላን ናቸው፡፡ በዚህ መካከል ንጉሱ ታመመና ሊሞት ተቃረበ፡፡ ለልኡላኑ፤ “ልጄ አዲሱ ዛር ነጋሲ(ንጉስ) እንዲሆን አድርጉ” አለ፡፡  ልኡላኑ ተቃወሙት፡፡ ያኔ ስልጣኑና አቅሙን እንደወሰዱበት ገባው፡፡ ወዳጅ ጠላቱን አወቀ፡፡
በዚያን ጊዜ ሩሲያ ዙሪያዋን ጠብ ተጭሮባት ነበር፡፡ እንዳጋጣሚ ግን እሱ ከሞት ዳነ፡፡ አንድ ጠዋት ማንንም ሳያሳውቅ የዛሩን መንግስት ሃብት ንብረት ይዞ ከቤተ-መንግስት ወጣ፡፡ አገሪቱ በድንገት ስጋት ላይ ወደቀች፡፡ ጥቂት ሰንብቶ ንጉሱ ደብዳቤ ላከ፤ “የልኡላኑንና የመሳፍንቱን ተንኮል ስላልቻልኩት ስልጣኔን ለቅቄያለሁ” አለ፡፡ ዜጋው፣ ነጋዴው፣ ሃብታሙ ግን ከጭንቀት ብዛት ዝም ብሎ ሊቀመጥ አልቻለም፡፡ ስለዚህ ያለበት ድረስ ሄዶ ተማጠነው፡፡ ንጉሱም ከብዙ ልመና በኋላ በመጨረሻ ሁለት ምርጫ ሰጣቸው፡፡ “ወይ ሙሉና ፍፁም ስልጣን ስጡኝ፡፡ ማንም ጣልቃ አይግባብኝ አልያ አዲስ መሪ ፈልጉ” አለ፡፡ አጣብቂኝ ውስጥ ከተታቸው፡፡
“አንተው ሁንልን!” አሉት፡፡ የበለጠ ስልጣን፣ የበለጠ ጉልበት አገኘና ቁጭ አለ፡፡ አጣብቂኝ ውስጥ የገባ፣ ሌላውን አጣብቂኝ ውስጥ በመክተት እራሱን ከአጣብቂኝ ያወጣል፡፡
ሀገር የፖለቲካና የኢኮኖሚ አጣብቂኝ ውስጥ ስትገባ፣ የፖለቲካ መሪዎችና ሃላፊዎች አጣብቂኝ ውስጥ ሲገቡ፣ የአስተዳደርና የአመራር አካላት አጣብቂኝ ውስጥ ሲገቡ፣ ዜጎች የኑሮ አጣብቂኝ ውስጥ ሲገቡ፤ አማራጭ መውጫ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የፖለቲካ አረንቋ ውስጥ ከገባን አማራጭ መውጫ ያሻናል፡፡ የኢኮኖሚ አዘቅት ውስጥ ከገባን አማራጭ ያሻናል፡፡ የጦርነት አዙሪት ውስጥ ከገባን (እንዲህ እንዳሁኑ) አማራጭ ያስፈልገናል፡፡ ሆኖም መብራት አጣን ለሚል ዜጋ፤ “ለምን ጄኔሬተር አይገጠምም” የሚል አማራጭ፤ ጥሩ አማራጭ አለመሆኑን መገንዘብ ያባት ነው፡፡ “መብራት ሳይኖር በፊት እንደኖረው ይኑር”፤ የሚል አማራጭም አማራጭ አይደለም፡፡ አማራጩ አማራጭ ብቻ ሳይሆን የመፍትሄ አማራጭ መሆን ይኖርበታል፡፡ ማህበረሰቡ “ዳቦ!” እያለ ይጮሃል ስትባል “ለምን ኬክ አይበሉም!” እንዳለችው እንደ ፈረንሳይዋ ንግስት እንደ ሜሪ አንቷሌት ያለ ታሪክ እንዳይደገም መጠንቀቅ ግድ ነው፡፡
ከአጣብቂኙ የሚወጡበት ሁነኛ መላም ያስፈልጋቸዋል፡፡ አማራጮችን ማየት ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ አማራጭ ሰዎች ያስፈልጋሉ፡፡ ብልህ አሳቢ ሽማግሌዎች ያስፈልጋሉ፡፡ ሆደ-ሰፊ ምሁራን ያስፈልጋሉ፡፡ ይህንንም እንደ አማራጭ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ አገርን የሚያድናት አማራጭ የመፍትሄ ሃሳብና አማራጩን ሃሳብ የሚያስፈፅም አማራጭ ሰው ነው፡፡ “ሁለት ባላ ትከል፣ አንዱ ቢሰበር በአንዱ ተንጠልጠል” የሚባለው ይሄኔ ነው!

በጋምቤላ ክልል የባሮ ወንዝ ሞልቶ ባስከተለው ጎርፍ፣ በጋምቤላ ከተማና በዘጠኝ ወረዳዎች በርካታ ሰዎችን እንዳፈናቀለ፣ የክልሉ መንግሥት ባለፈው ማክሰኞ አስታውቋል፡፡
የጋምቤላ ከተማ ጤና ጽሕፈት ቤት ኃላፊና የከንቲባው ተወካይ አቶ ሳይመን ቲያቺ፣ ባለፉት አራት ቀናት ውስጥ ስድስት ሺ  የሚደርሱ ሰዎች ተፈናቅለው በትምህርት ቤቶችና በደረቃማ አካባቢ ላይ እንደሚገኙ፣ ለአሜሪካ ድምፅ ገልጸዋል።
በደረሰው የጎርፍ አደጋ ንብረት እንደወደመና በእንስሳት ላይም ጉዳት እንደደረሰ የጠቆሙት የከንቲባው ተወካይ አቶ ሳይመን፤ እስካሁን በጎርፉ የሰው ህይወት አለማለፉን ተናግረዋል፡፡
የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ተወካይና የሰላምና ጸጥታ ቢሮ ምክትል ሃላፊ አቶ ኡሞድ ኡሞድ  በበኩላቸው፣ የክልሉ ህዝብ ወንዞችን እየተከተለ የሰፈረ ነው፣ በመሆኑም የባሮ፣ የአልዌሮ፣ የጊሮና የአኮቦ ወንዞች በከባድ ዝናብ ምክንያት ሞልተው በመፍሰስ፣ በዘጠኝ ወረዳዎች ውስጥ ጎርፍ ማስከተላቸውን ገልጸዋል፡፡
አቶ ኡሞድ እንዳሉት፤ በኑዌር ዞን አምስቱም ወረዳዎች፣ የክልሉን ዋና ከተማ ጨምሮ በጎርፉ እጅጉን ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡ የ01፣ 02፣ 04 እና 05 ቀበሌዎች ነዋሪዎች በጎርፉ ከብቶቻቸውንና ንብረቶቻቸውን አጥተዋል፡፡ የባሮ ወንዝ መጨመር ተጨማሪ የአደጋ ስጋት መደቀኑን የቀጠለ ሲሆን፤ መንግሥት ለችግሩ ጊዜያዊና ዘላቂ መፍትሄ እንዲሰጠው ነዋሪዎች ጠይቀዋል።
በጋምቤላ ከተማ የተከሰተው ጎርፍ በዚህ መጠን ህብረተሰቡን ያፈናቀለው ከ15 ዓመት በፊት በ2000 ዓ.ም እንደነበር ያስታወሱት አንድ የከተማው ነዋሪ፤ የባሮ ወንዝ በሞላ ቁጥር ዳግም ህብረተሰቡን እንዳያፈናቅል መንግስት ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት መረጃ መሠረት፤ ባለፈው ዓመት ከነሐሴ ወር መጀመሪያ አንስቶ እስከ ጥቅምት ወር የጣለውን ከፍተኛ ዝናብ ተከትሎ፣ በ12 ወረዳዎች እንዲሁም በጋምቤላ ክልላዊ መንግሥት ዋና ከተማ በተከሰተው ጎርፍ 76ሺ631 ሰዎች ለጉዳት ተዳርገው ነበር፡፡
በተመሳሳይ፣ በኦሮሚያ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች፣ የክረምቱ ዝናብ የሚያስከትለው ጎርፍ፣ ከ270ሺሕ በላይ ሰዎች ላይ ጉዳት ሊያስከትል እንደሚችል፣ በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብአዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ(ኦቻ) ባለፈው ሳምንት  አመልክቷል።





”በኢትዮጵያ የድህረ-ምርት ብክነቱ ወደ 25 ሚ. ገደማ ህዝብ የሚመግብ ነው“


ባለፈው ማክሰኞ መስከረም 8 ቀን 2016 ዓ.ም እዚህ አዲስ አበባ በአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን አዳራሽ የተከፈተው አራተኛው የመላው አፍሪካ ድህረ-ምርት ኮንግረስና ኤግዚቢሽን፣ ”ዘላቂ የድህረ-ምርት አመራር፡ የአፍሪካን የእርስ በእርስ የግብርና ንግድ ማሳደግና የምግብና ሥነምግብ ዋስትናን ማጎልበት“ በሚል ጭብጥ፣ እስከ ትላንት  አርብ  ድረስ ለአራት ቀናት ተካሂዷል፡፡  
ኮንግረሱ በአፍሪካ አህጉር እጅግ ወሳኝ የሆነውን የምግብና ውሃ ብክነት ችግር መፍትሄ ለማበጀት ያለመ ነው ተብሏል፡፡
በኮንግረሱ ላይ ለውይይት ከቀረቡ ርዕሰጉዳዮች መካከል፡- ዘላቂ የድህረ-ምርት አሰራሮች፣ የምርት ብክነትን የሚቀንሱ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎች፣ ብክነትን ለመከላከል የሚያግዙ ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎች እንዲሁም የመፍትሄ ሃሳቦችን ለማስፋት አጋርነትን ማጠናከር የሚሉ ይገኙባቸዋል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በኮንግረሱ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት በአፍሪካ ህብረት የግብርና፣ የገጠር ልማት፣ የብሉ ኢኮኖሚና ዘላቂ ከባቢ ኮሚሽነሯ ክብርት ጆሴፋ ሊዎኔል ኮሬያ ሳኮ፤ “በዓለማቀፍ ደረጃ የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ የጋራ ጥረት ብናደርግም፣ የእህል ብክነት በተለይም የድህረ-ምርት ብክነት በአፍሪካ የልማት ተግዳሮት ሆኖ ቀጥሏል፤ ይሄ ደግሞ  የምግብ ዋስትና አለመረጋገጥ  ችግርን ያባብሳል፣ የገበሬዎችንና ማህበረሰቦችን ገቢ ይቀንሳል፣ ውዱን የመሬት፣ ውሃና ኢነርጂ ሃብትን በከንቱ እንዲባክን ያደርጋል..” ብለዋል።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የምግብና ሥነ-ምግብ ተባባሪ ፕሮፌሰር አሻግሬ ዘውዱ (ዶ/ር) በሰጡት ሙያዊ ማብራሪያ፤ የኢትዮጵያ ድህረ ምርት ብክነት በእህል እስከ 30%፣ በአትክልትና ፍራፍሬ ደግሞ እስከ 70% እንደሚደርስ ጠቁመው፤ የምርት ብክነቱ ወደ 25 ሚሊዮን ገደማ ህዝብ የሚመግብ ነው ብለዋል።
አፍሪካውያን ምርታችንን እርስ በርስ ስለማንገበያይ ከፍተኛ ብክነት ይከሰታል የሚሉት ተባባሪ ፕሮፌሰሩ፤ እስያውያን እስከ 60% ድረስ ሲገበያዩ፣ አፍሪካውያን ግን እስከ 20% ብቻ ነው የሚገበያዩት፤ ሲሉ አብራርተዋል፡፡
የምግብ ብክነት ዓለማቀፍ ክስተት እንደመሆኑ መጠን፣ አንድ ጥናት እንደሚያሳየው፣ በዓለም ላይ ለሰው ልጅ ፍጆታ ከሚመረተው ምግብ 30 በመቶ ገደማ የሚሆነው በከንቱ ይባክናል፡፡
የተባበሩት መንግሥታት የምግብና እርሻ ድርጅት (FAO) እ.ኤ.አ በ2019 ባወጣው መረጃ መሰረት፣ የምግብ ብክነቱ በገንዘብ ሲመነዘር፣ በበለጸጉት አገራት በየዓመቱ ወደ 680 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ሲሆን፤ በታዳጊ አገራት ደግሞ 310 ቢሊዮን ዶላር ገደማ እንደሚያህል ተገምቷል፡፡  
አራተኛውን የመላ አፍሪካ ድህረ-ምርት ኮንግረስና ኤግዚቢሽን፣ የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ከተለያዩ የልማት አጋሮች፣ የግል ዘርፉ ተዋናዮች፣ የምርምር ተቋማትና የሲቪል ማህበረሰብ ተወካዮች ጋር በመተባበር እንዳዘጋጀው ታውቋል፡፡



Page 12 of 676