Administrator

Administrator

 · “አገሪቱ ጭንቀት ላይ እያለች መጸለይ እንጂ መጉላላት አይገባችሁም”
            - ኮሚሽነር ዶ/ር አዲሱ ገ/እግዚአብሔር
     · “ሙስናን ቀጣዩ ትውልድ ይቀርፈው ይሆናል” - ፓትርያርክ አባ ማትያስ

   የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን፣ በኢ/ኦ/ተ/ቤተክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም ያይኑን በጽ/ቤቱ ጠርቶ፣ ከቤተ ክርስቲያን በሕገ ወጥ መንገድ በተባረሩ 250 ያህል አገልጋዮችና ሠራተኞች የመብት ጥሰት ጉዳይ አነጋገረ፡፡
የኮሚሽኑ ኮሚሽነር ዶ/ር አዲሱ ገ/እግዚአብሔር፤ የሀገረ ስብከቱን ሥራ አስኪያጅ ከትላንት በስቲያ ኀሙስ በጽ/ቤታቸው ጠርተው ባነጋገሩበት ወቅት፣ የካህናቱ አቤቱታ ተቀባይነት እንዳለው አስታውቀው፤ በአጭር ጊዜ ውስጥ መፍትሔ እንዲሰጣቸው አሳስበዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የተለያዩ አድባራት ጥቅማችን ሳይጠበቅ፣ ጉዳያችን በአግባቡ ሳይመረመር በሕገ ወጥ መንገድ ታግደናል፣ ተሰናብተናል፣ ተዛውረናል፤ ሲሉ ለኮሚሽኑ ያመለከቱት 250 ያህል ካህናትና ልዩ ልዩ ሠራተኞች፣ በሀገረ ስብከቱ ያለውን የመልካም አስተዳደር እና የሙስና ችግር በማጋለጣችን በደል ተፈጽሞብናል ብለዋል - ለኮሚሽኑ በጽሑፍ ባቀረቡት አቤቱታ፡፡
ይህን የካህናቱንና የሠራተኞችን አቤቱታ የተቀበለው ኮሚሽኑ፤ ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሓላፊዎች ጋር ለአራት ሰዓታት በጉዳዩ ላይ እንደተነጋገረ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የሥራ ሓላፊዎቹን በተናጠል ኮሚሽኑ ካነጋገረ በኋላም ከአቤቱታ አቅራቢዎቹ ጋር በመሆን በጉዳዩ ላይ መወያየታቸው ታውቋል፡፡
ኮሚሽነር ዶ/ር አዲሱ ገ/እግዚአብሔርም ለአቤቱታዎቹ መፍትሔ እንደሚሰጡ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ቃል እንደገቡላቸው በመጠቆም፤ “ሀገሪቱ ጭንቅ ላይ እያለች መጸለይ እንጂ መጉላላት አይገባችሁም፤ ጉዳያችሁ በአጭር ጊዜ መፍትሔ ያገኛል፤” ብለዋል- በስብሰባው የተሣተፉ ካህናት ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት፡፡
የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም፤ አቤቱታ አቅራቢዎቹ እንደ ቅሬታቸው እየታየ ምላሽ ይሰጣቸዋል፤” ያሉ ሲሆን፣ አቤቱታ አቅራቢዎቹ ግን፤ የችግሩ ፈጣሪ ከሆነው የሀገረ ስብከቱ አመራር የምንጠብቀው መፍትሔ የለም፤ ብለዋል፡፡
አክለውም፤ “ገለልተኛ አካል ተቋቁሞ ጉዳያችን እንዲጣራ እንጂ ሀገረ ስብከቱ ችግሩን የመፍታት አቅም የለውም፤” ሲሉ  በአስተዳደሩ ተስፋ መቁረጣቸውን ገልጸዋል፡፡
ኮሚሽነር ዶ/ር አዲሱ በበኩላቸው፤ ሀገረ ስብከቱ ለአንድ ጊዜ ዕድል ይሰጠውና መፍትሔውን ያብጅ፤ የሚል ውሳኔ መስጠታቸው ታውቋል፡፡
የአዲስ አበባ ሀገረ ሰብከትን በበላይነት የሚመሩት ፓትርያርክ አባ ማትያስ፣ በዓለ ሢመታቸውን ምክንያት በማድረግ በቅርቡ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ቴሌቭዥን ጣቢያ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ የሙስና ጉዳይ ከ5 ዓመት በፊት ቀላል መስሎኝ ነበር፤ ነገር ግን በኋላ ቀላል እንዳልሆነ ተረድቻለሁ፤ ብለዋል፡፡
ሙስናው በኔትወርክ የተሳሰረና እንደ ሸረሪት ድር ያደራ መሆኑን በመጥቀስም፣ በሀገረ ስብከቱ መጠነኛ ለውጥ ቢታይም ሙስና አሁንም መንሰራፋቱን ጠቁመው፤ “ምናልባት በቀጣይ ትውልዱ ይቀርፈው ይሆናል፤” በማለት ተስፋቸውን ገልጸዋል፡፡

“በሞያሌ የተፈፀመው ግድያ በስህተት አይደለም” ያሉት የኦሮሚያ ፍትህ ቢሮ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ታዬ ደንደኦ፣ ከትላንት በስቲያ ሐሙስ ጠዋት፣ በኮማንድ ፖስት ተይዘው መታሰራቸው ታውቋል፡፡
አቶ ታዬ ባለፈው ቅዳሜ በሞያሌ ከተማ 10 ሰዎች በመረጃ ስህተት በሚል በመከላከያ ሃይል ሰራዊት ተተኩሶ መገደላቸውን ተከትሎ ለቪኦኤ እና ለጀርመን ድምፅ ራዲዮ በሰጡት መግለጫ፤የኦሮሚያ ፍትህ ቢሮ ግድያው በመረጃ ስህተት የተፈፀመ ነው ብሎ እንደማያምን ማስታወቃቸው  አይዘነጋም፡፡
ኃላፊው በመግለጫቸው ግድያውን ፈፅመዋል በሚል በቁጥጥር ስር የዋሉት የመከላከያ ሰራዊቱ አባላት፣ በወታደራዊ ፍ/ቤት ይዳኛሉ መባሉን በመቃወም፣ ህዝብ በግልፅ ሊከታተለው በሚችለው የክልሉ መደበኛ ፍ/ቤት ጉዳያቸው መታየት አለበት ሲሉም ተከራክረዋል፡፡  
አቶ ታዬ ደንደኦ ሐሙስ ጠዋት አዲሱ ገበያ አካባቢ ከሚገኘው መኖርያ ቤታቸው፣ ወደ ቢሮአቸው ሲያመሩ፤ በፌደራል ፖሊስ አባላት መያዛቸውን የአይን እማኞች ገልፀዋል፡፡ አቶ ታዬ ሲታሰሩ የአሁኑ ለሦስተኛ ጊዜ መሆኑን የሚገልጹት ምንጮች፤ከዚህ ቀደምም ለ3 ዓመትና ለ7 ዓመታት መታሰራቸውን ያስታውሳሉ፡፡   
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማስፈፀሚያ መመሪያ፤የክልል መንግስታት የኮሙኒኬሽን ኃላፊዎችና ባለስልጣናት በጸጥታ ጉዳዮች ላይ መግለጫ እንዳይሰጡ የሚከለክል መሆኑ ይታወቃል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ከታወጀ ወዲህ በኦሮሚያ ክልል አቶ ታዬ ደንደኦን ጨምሮ የኦሮሚያ ፖሊስ ኮሚሽን የአድማ በታኝ ኃይል አዛዥ፣ የነቀምት ከተማ ከንቲባ፣የምስራቅ ወለጋ ዞን ም/አስተዳዳሪና የከለም ወለጋ ወረዳ ፍትህ ቢሮ ሃላፊ በኮማንድ ፖስቱ መታሰራቸውን ምንጮች ይናገራሉ፡፡
እስካሁን በኮማንድ ፖስቱ ማንና ምን ያህል ግለሰቦች እንደታሰሩ ያልተገለጸ ሲሆን የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን ለመቆጣጠር በፓርላማ አባላት የተቋቋመው የምርመራ ቦርድ፣በሚቀጥለው ሳምንት መጀመሪያ ላይ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የታሰሩትን አካላት ስም ዝርዝር  ይፋ እንደሚያደርግ ይጠበቃል፡፡   

  “በመልካም አስተዳደርና በፍትህ እጦት እየተንገላታን ነው”

     ያለ አግባብ ከቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪነታችን ተባረናል፣ ደሞዝም ተቋርጦብናል ያሉ ካህናት፤ በፍ/ቤት ተከራክረን ብንረታም ፍርዱ ሳይፈፀምልን እየተጉላላን ነው ሲሉ ምሬታቸውን ገልጸዋል፡፡
መልአከ ገነት ኃ/ማሪያም ቦጋለ እና መጋቢ ሃይማኖት መንግስቱ ድረስ፣ በ2009 ዓ.ም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ የአዲስ አበባ ሃገረ ስብከት መንፈሳዊ ፍ/ቤት ባቀረቡት አቤቱታ፤ከህግ አግባብ ውጪ ከስራቸው መባረራቸውንና ደሞዛቸውን ተከልክለው ለችግር መዳረጋቸውን የገለጹ ሲሆን ፍ/ቤቱም አቤቱታቸው ተገቢነት ያለው ነው ብሎ ወደ ስራ መደባቸው እንዲመለሱ፣ደሞዝም እንዲቆረጥላቸው ውሳኔ ማሳለፉን ይናገራሉ፡፡  
የፍ/ቤቱ ውሳኔ በሚያዚያ 2009 ዓ.ም የተሰጠ ቢሆንም እስከ ዛሬ ድረስ ለዓመት ገደማ ተፈጻሚ እንዳልሆነ ለአዲስ አድማስ የጠቆሙት ካህናቱ፤በአዲስ አበባ ሃገረ ስብከት ከፍተኛ በደል እየተፈፀመብን ነው ብለዋል፡፡ ጉዳያቸው ፈጣን እልባት እንዲያገኝ ለፓትርያርክ ፅ/ቤት አመልክተው የፍ/ቤቱ ውሳኔ በአስቸኳይ እንዲፈፀምላቸው ትዕዛዝ ቢሰጥም እስካሁን በትዕዛዙ መሰረት ወደ ሥራቸው አለመመለሳቸውን ተናግረዋል - ካህናቱ፡፡   
 የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን በጉዳዩ ጣልቃ እንዲገባ አቤቱታ ማቅረባቸውንም የጠቆሙት ካህናቱ፤ኮሚሽኑ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ነሐሴ 1 ቀን 2009 ዓ.ም በፃፈው ደብዳቤ፤ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ እንዲከበርና ካህናቱ ወደ ስራ መደባቸው እንዲመለሱ በማሳሰብ፣ይህ ሳይሆን ከቀረ ትዕዛዙን ባልፈፀሙት ወገኖች ላይ የህግ እርምጃ እንደሚወሰድ ቢገለፅም ይህም ተቀባይነት አላገኘም ብለዋል፡፡
ከዚህ በኋላ ጉዳያችንን ወዴት አቤት እንደምንል አናውቅም የሚሉት ካህናቱ፤በመልካም አስተዳደርና በፍትህ እጦት እየተንገላቱ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡  

• የምተዳደረው በሙዚቃ ሳይሆን በሂሳብ ባለሙያነቴ ነው
• እዚህ አገር የሙዚቃ ህይወት በጣም ፈታኝ ነው

ከ10 ዓመት በፊት አልበም ለማሳተም ከኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ጋር ተዋውሎ የነበረ ቢሆንም ሳይሳካለት ቀርቷል፡፡ ከዚያ ወዲህ ግን አምስት ነጠላ ዜማዎችን በመልቀቅ ዕውቅንና ተወዳጅነትን አግኝቷል፡፡ በመጨረሻ የለቀቀው “ተመለሽ” የተሰኘው ባህላዊ ዘፈኑ በእጅጉ ከመወደዱ የተነሳ በዩቲዩብ ከ1 ሚሊዮን በላይ ተመልካች ያገኘ ሲሆን በዚህ ዘፈን ምክንያትም በአውሮፓ የተለያዩ ከተሞች ኮንሰርቶች እንዲሰራ ግብዣ ቀርቦለት፣ ለጉዞው እየተዘጋጀ ይገኛል፡፡ የዛሬው የአፍታ ቆይታ እንግዳችን የሂሳብ ባለሙያና ድምጻዊ አያሌው ንጉሴ (ያዩ)፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከድምጻዊው ጋር የአፍታ ቆይታ አድርጋለች፡፡

እንዴት ነው ወደ ሙዚቃ የገባኸው?
ሙዚቃን በት/ቤት ሚኒ ሚዲያና በቤተሰብ መምሪያ ነው የጀመርኩት፡፡ ከዚያ በኋላ ቀስ በቀስ ወደ ሙያው በጥልቀት ልገባ ችያለሁ፡፡ ከዚያ በፊት ቤት ውስጥ በጣም ሙዚቃ አዳምጥ ነበር፡፡ ቤት ውስጥ ተገዝተው የሚመጡ ካሴቶችን እየከፈትኩ እያዳመጥኩ፣ አብሬ እያንጎራጎርኩ ነው ይበልጥ ወደ ሙዚቃው የተሳብኩት፡፡
መድረክ ላይ የማቀንቀን ዕድል ያገኘኸው እንዴት ነው?
ወደ ትልልቅ መድረክ መጣሁ የምለው እንግዲህ ከኤክስፕረስ ባንዶች ጋር ነው፡፡ የተለያዩ ባዛሮች ላይ በመጋበዝና በመዝፈን ነው እራሴን እያሳደግኩ የመጣሁት፡፡
ብዙ ወጣት ድምፃዊያን ወደ መድረክ ሲመጡ መጀመሪያ ላይ የአንጋፋ ድምፃዊያንን ዘፈን በመዝፈንና በምሽት ክበቦች ድምፃቸውን በመግራት ነው፡፡ በዚህ በኩል ያንተ ልምድ ምን ይመስላል?
በክለብ ደረጃ የቴዎድሮስ ታደሰንና የጥበቡን ሥራዎች እጫወት ነበር፡፡ በማድነቅ ደረጃ እነዚህን ድምፃዊያን አደንቃለሁ፡፡ ከሴቶች የፍቅርአዲስ አድናቂ ነኝ፡፡ ባህላዊ ዘፋኝ እንደመሆኔ፤ መሰረት በለጠንም በጣም አደንቃታለሁ፡፡ የሰራሁባቸው የምሽት ክበቦች ዋሊያ የሚባል ልደታ አካባቢ የነበረ ቤት፣ ቦሌ ደግሞ አበጋዝ የሚባል ምሽት ክበብ ሰርቻለሁ፡፡ አዲስ አበባ ብቻ ወደ ሶስትና አራት የምሽት ቤቶች ሰርቻለሁ፡፡ በዚህም በርካታ ልምዶችን ቀስሜያለሁ፡፡
በሙዚቃ ህይወትህ ፈታኝ የምትለው ወቅት አለ?
እዚህ አገር በአጠቃላይ የሙዚቃ ህይወት በጣም ፈታኝ ነው፡፡ ከፈታኝነቱም አልፎ አስቀያሚ ነው፤ ግን ታግሰሽ ካለፍሽ ፍሬው ደስ ይላል፡፡ ያንን ፍሬ ለማየት ከፍተኛ ትዕግስትና ተስፋ አለመቁረጥ ግን የግድ ነው፡፡ ጥንካሬው ከሌለ ሙያውን ጠልተሽ ሁሉ ጥለሽ ልትወጪ ትችያለሽ፡፡
ከ10 ዓመት በፊት አልበም ለማሳተም ከኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ጋር ስምምነት ላይ ደርሰህ እንደነበር ሰምቻለሁ፡፡ እስካሁን ታትሞ ለአድማጭ ያልበቃበት ምክንያት ምንድን ነው?
እንግዲህ ለሙዚቃው ካለኝ ፍቅር የተነሳ ገና ተማሪ ሆኜ፣ በ1995 ዓ.ም አካባቢ ነው አልበም መስራት የጀመርኩት፡፡ እሱን ስጀምር ተማሪ እንደ መሆኔ በቤተሰብ ገንዘብ ነበር የጀመርኩት። ያኔ ስቱዲዮ ለመግባት በጣም ውጣ ውረድ ነበረው፡፡ እንዲያም ሆኖ አልበሙ አልታተመም። አልበሙ እንዲታተም ስምምነት ያደረግኩት ከኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ጋር ነበር፡፡ ከዚያ የሙዚቃ ቤት ባለቤቱ፣ አምስት ዘፈኖች መርጠው አወጡና፣”እነዚህ አይሆኑም ቀይር” አሉኝ፡፡
ከዚያስ?
እንደነገርኩሽ ተማሪ ስለነበርኩ ከቤተሰብ የምሳና የትራንስፖርት እየተቀበልኩ፣ ከደብረዘይት አዲስ አበባ ተመላልሼ ነው፣ ስቱዲዮ እየገባሁ ሰርቼ የጨረስኩት፡፡ ከዚያ ሁሉ ችግር በኋላ አምስት ዘፈን ቀይረሽ፣ ግጥምና ዜማ አሰርተሽ፣ እንደገና ስቱዲዮ መግባት ለእኔ በዛን ወቅት በጣም ከባድ ስለነበር በዚህ ምክንያት ቀረ፡፡
አሁን አቅም ካገኘህ በኋላስ ለምን አላሳተምከውም?
አሁን ስታይው ሁሉም ነገር ተቀይሯል፤ ቴክኖሎጂው --- ቅንብሩ --- ከ10 ዓመት በፊት ያለውና የአሁኑ አይገናኝም፡፡ በዚህ ምክንያት ሳይታተም ቀረ ማለት ነው፡፡
እስኪ ስለተወዳዱልህ ነጠላ ዜማዎችህ ትንሽ አጫውተኝ?
መጀመሪያ ላይ ስለ መርሀቤቴ የሚገልፅ “መሬው” የተሰኘ ነጠላ ዜማ ነው የለቀቅኩት፡፡ ዜማና ግጥሙን እኔ ሰርቼ፣ ቅንብሩን ሙሃዘ ፀጋዬ ሰራው፤ ሚክሲንጉ በኤክስፕረስ ባንዱ ክብረት ዘኪዎስ ነበር የተሰራው፡፡ በመቀጠል “ድንገት መጣሽብኝ” የተሰኘውን ነጠላ ዜማ ለቀቅኩኝ፡፡ ዜማውን እኔ ነኝ የሰራሁት፡፡ ቅንብሩን አማኑኤል ይልማ የሰራው ሲሆን ግጥሙ የአንጋፋው ገጣሚ ግሩም ሀይሌ ነው፡፡ ግሩም ሀይሌ እጅግ የማደንቃቸውና የማከብራቸው ባለሙያ ናቸው፡፡ በዚህ ዘፈንም ጥሩ እውቅናና ተቀባይነት አግኝቻለሁ፡፡ “የከበርሽ እንቁ” የተሰኘ ሌላው ስራዬ ጎንደር የተቀረፀ፣ የጎንደር ባህልና ትውፊትን ጠብቆ የተሰራ ስራ ነው። ዳይሬክተሩ ስንታየሁ ሲሳይ ነው፤ ይህ ነጠላ ዜማ ከ130 ሺህ ብር በላይ ወጥቶበታል፡፡ ዜማና ቅንብሩን የሰራው አሌክስ ይለፍ ነው፡፡ ይህም ዘፈን እጅግ የተዋጣላት ነበር፡፡
በ2009 ዓ.ም መስከረም ላይ “ተመላሽ” የሚል ዘፈን ሰራሁ፡፡ ከዚህ በፊት ሀብተሚካኤል ደምሴ ነፍሳቸውን ይማርና ሰርተውት ነበር፡፡ ዜማውን የሰራው የኔው አካሉ ነበር፤ አስፈቅጄ አስፈላጊውን ክፍያ ፈፅሜ፣ አዲስ ግጥም በግሩም ሀይሌ አሰርቼ ለቀቅኩት፡፡ ይሄ ዘፈን በጣም ነው የተወደደው፡፡ በዩቲዩብ ከ1. ሚሊዮን በላይ ሰው ተመልክቶታል፤ ገብቶ ማየት ይቻላል፡፡
ይሄ ዘፈን በአውሮፓ ከተሞች ኮንሰርት የመሥራት ግብዣ አስገኝቶልሃል---
በትክክል፡፡ አሁን፤ ከሁለት ወራት በኋላ በአውሮፓ የተለያዩ ከተሞች ለአንድ ዓመት የሚቆይ ኮንሰርት ለመስራት በዝግጅት ላይ ነኝ፡፡ በአገር ውስጥም የተለያዩ ኮንሰርቶችን ለመስራት ግብዣዎች ቀርበውልኛል፡፡
ከሙዚቃው ውጭ የሂሳብ ባለሙያም ነህ …
አዎ፤ እውነት ነው፡፡ በአካውንቲንግ ሙያ በመንግስት መሥሪያ ቤት እየሰራሁ እገኛለሁ። የምተዳደረውና የምኖረው በዚህ ሙያዬ እንጂ ከሙዚቃው እስካሁን ያገኘሁት ጥቅም የለም፡፡ ወደፊት ነው ውጤቱን የማየው፡፡
በሂሳብ ባለሙያነትህ የተከበርክና የተዋጣልህ ነህ፡፡ ሙዚቃው በመንግስት ሥራህ ላይ ጫና አያሳድርብህም?
ይሄኛውንም ስራዬን በአግባቡ ነው የምሰራው፤ ምክንያቱም የምተዳደረው በሙዚቃው ሳይሆን በዚህኛው ሙያዬ ነው፡፡ ነገር ግን በመስሪያ ቤት ያሉ ጓደኞቼም አለቆቼም ለሙዚቃው ያለኝን ፍቅር ስለሚያውቁ በደንብ ይረዱኛል፡፡ ሙዚቃ በአብዛኛው ሌሊት ነው የሚሰራው፡፡ በዚያ ላይ አዲስ አበባ ተመላልሼ ነው የምሰራው፡፡ ሌሊት ሰርተሽ ጠዋት ደክሞሽ ጠውልገሽ ነው ሥራ የምትገቢው፡፡ ድካም በሚያጋጥመኝ ጊዜ አለቆቼና ጓደኞቼ ሥራዬን ሸፍነው እንዳርፍ ያደርጋሉ፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለመስሪያ ቤት አለቆቼና ጓደኞቼ ከፍ ያለ ምስጋና ማቅረብ እፈልጋለሁ፡፡
የአገሪቱን የሙዚቃ ኢንዱስትሪ እንዴት ትገልጸዋለህ?
የአገሪቱ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ በጣም ከባድና አስቸጋሪ ነው፡፡ አንደኛ፤ ኢንዱስትሪው በተወሰኑ ሰዎችና በቲፎዞዎቻቸው የተያዘ ነው፡፡ ሁለተኛ፤ ለፍተሽ ደክመሽ፣ ለአንድ ነጠላ ዜማ ቪዲዮ ከመቶ ሺህ ብር በላይ እያወጣሽ፣ ሚዲያዎች አንቺን ለማበረታታትና ሥራሽ ለሰው እንዲደርስ ለማድረግ ፈቃደኛ አይሆኑም፡፡ ቲፎዞ አጃቢ ሊኖርሽ ይገባል። ወዲህ ደግሞ የቅጂ መብት አለመከበር አለ፡፡ ይሄ ሁሉ ተደማምሮ ዘርፉ ከባድ እንዲሆን አድርጎታል። ሆኖም ስራውን ስለምንወደው እንቀጥልበታለን። እንደ አዲስ ሙዚቃውን ለሚቀላቀሉ ጀማሪዎች፣ መስመሩ በጣም የተጣበበ ነው፡፡
በሙዚቃው ዘርፍ ህልምህ ምንድን ነው?
የእኔ ህልም የግል የሙዚቃ ት/ቤት መክፈት ነው፡፡ ፍላጎቱም ተሰጥኦውም ኖሯቸው፣ መንገዱንና አካሄዱን አጥተው፣ ከእነ ህልማቸው የተቀመጡ ድምፃዊያንን ወደ አደባባይ ማውጣትና ዕድል መስጠት እፈልጋለሁ፡፡ እኔ ዛሬ እነዚህን ክሊፖች ሰርቼ ህዝብ ጋ ለመድረስ እጅግ ብዙ ውጣ ውረዶችን አልፌያለሁ፡፡ በአሁኑ ሰዓት መንገዱን አጥተው፣ ብቃታቸውን ይዘው የተቀመጡ፣
ምን ያህል ወጣቶች እንዳሉ ቤት ይቁጠራቸው።
ከ10 ዓመት በፊት ተሰርቶ ሳይታተም የቀረው አልበምህ ዕጣ ፈንታው ምንድን ነው?
እንደነገርኩሽ የዘመኑ ቴክኖሎጂ ክፍተት አለ፤ እነሱን አስተካክዬ ለመስራት ስቱዲዮ ገብቻለሁ። ነገር ግን ቶሎ ለማጠናቀቅ በቂ ጊዜ የለኝም፡፡ አንድም የመንግስት ሰራተኛ ነኝ፤ ሁለትም አሁን የውጭ ጉዞ ሂደት ጀምሬያለሁ፤ በመላው አውሮፓ ነው ኮንሰርት የምሰራው፡፡ አልበሙ ሁኔታዎች ሲፈቅዱ በደንብ ተሰርቶ ለአድማጭ ይቀርባል፡፡
እንዴት ነው ለደብረዘይት አልዘፈንክም?
እንግዲህ ተወልጄ ያደግሁባት ከተማ በመሆኗ በጣም እወዳታለሁ፡፡ ለዚህም ደብረዘይትን የሚያወድስ ኦሮምኛ በአማርኛ የሆነ ዘፈን ከፀጋዬ ደንደና ጋር ለመስራት አስቤያለሁ፤ ዜማው አልቋል፡፡ ግጥሙን ፀጋዬ እየሰራ ነው፡፡ ከቻልኩ ወደ ውጭ ከመሄዴ በፊት ካልተቻለ ስመለስ እለቀዋለሁ ብያለሁ፡፡ በውጭ ጉዞዬም አንድ ሁለት ነጠላ ዜማዎችን ለመልቀቅ አስቤያለሁ፤ ስመለስም አልበሜን እየሰራሁ ነጠላ ዜማዎችን በተከታታይ በመልቀቅ በደንብ ወደ ህዝቡ ዘልቄ ለመግባት እፈልጋለሁ፡፡ እንግዲህ እግዚአብሔር ፈቃዱ ይሁን፡፡ በዚህ አጋጣሚ ጋዜጣችሁ እንግዳ ስላደረገኝ በጣም አመሰግናለሁ፡፡ በስራ ቦታዬ ያሉ ጓደኞቼን፣ አብሮ አደጎቼን፣ ወላጆቼን ባለቤቴን መሰረት ተስፋን፣ አቀናባሪዎቼን፣ ግጥምና ዜማ የሚሰሩልኝን ሁሉ ላመሰግን እወዳለሁ፡፡ ከምንም በላይ ኃያሉ እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ፡፡

80ኛው ዙር “ግጥም በጃዝ” የኪነ - ጥበብ ምሽት የፊታችን ረቡዕ መጋቢት 5 ቀን 2010 ዓ.ም ከቀኑ 11፡30 ጀምሮ በራስ ሆቴል ይካሄዳል፡፡
በዕለቱ ገጣሚና ጋዜጠኛ ነብይ መኮንን ረዳት ፕሮፌሰር ነብዩ ባዬ፣ የትነበርሽ ንጉሴ፣ ሎሬት አዳነች ወ/ገብርኤል፣ ምልዕቲ ኪሮስ፣ ትዕግስት ማሞና ምስራቅ ተረፈ ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን በዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ የተደረሰ አጭር ተውኔት በአርቲስት ሽመልስ አበራና እታፈራሁ መብራቱ ለታዳሚ እንደሚቀርብም ታውቋል፡፡

ጋለሪያ ቶሞካ 25ኛውን ዙር የስዕል ትርኢት ትላንት ምሽት ሳር ቤት ካናዳ ኤምባሲ ፊት ለፊት በሚገኘው ጋለሪው የከፈተ ሲሆን ለሁለት ወራት ለዕይታ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡
በዚህ ትርኢት ላይ የአንጋፋዋ ሰዓሊ ስናፍቅሽ ዘለቀ ከ40 በላይ ስራዎች “ራስን ፍለጋ” በሚል ርዕስ ለእይታ ይቀርባሉ ተብሏል፡፡

በናይጄሪያ 1ኛ የሚወጣ አሸናፊ ግማሽ ሚሊዮን ብር ይሸለማል

በዲያጂዮ ስር የሚመረተው ማልታ ጊነስ፤ “ማልታ ቬተር” በተባለና በአራት የአፍሪካ አገራት መካከል ለሚደረግ የተለያዩ አዝናኝና ስፖርታዊ ውድድሮች ለመጨረሻ ዙር ያለፉ 10 ኢትዮጵያውያን ወጣቶችን ወደ ናይጄሪያ ሊልክ ነው፡፡ በናይጄሪያ ሌጎስ በሚደረገው በዚህ ውድድር አንደኛ የሚወጣ አሸናፊ 20 ሺህ ዶላር (ግማሽ ሚሊዮን ብር) እንደሚሸለም የማልታ ጊነስ ብራንድ ማናጀር ወ/ሪት ረድኤት ዘገየ ባለፈው ሰኞ በጎልደን ቱሊፕ ኢንተርናሽናል ሆቴል በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡
በዚህ ውድድር የጋና የአይቬሪኮስት፣ የናይጄሪያና የኢትዮጵያ ወጣቶች የሚሳተፉ ሲሆን ውድድሩ ብዙ ክህሎቶችን የማይጠይቅና ቀላል በሚመስሉ ጨዋታዎችና ስፖርታዊ ውድድሮች የተሻለና ፈጣን ፈጠራን በመጠቀም የአስተሳሰብ አድማስን የሚያሰፋ እንደሆነም ተገልጿል፡፡
ውድድሩ ከህዳር 2010 ዓ.ም ጀምሮ በኢትዮጵያ በተከታታይ ሲካሄድ መቆየቱንና በየዙሩ እያሸነፉ ለመጨረሻው ዙር ያለፉት ስድስት ወንዶችና አራት ሴት ወጣቶች ከየካቲት 30 ጀምሮ ለ10 ተከታታይ ቀናት በናይጄሪያ ሌጎስ በሚደረግ ውድድር የሚሳተፉ ሲሆን አሸናፊው ግማሽ ሚሊዮን ብር እንደሚሸለም ኃላፊዎቹ ተናግረዋል፡፡

የጀርመን የባህል ማዕከል (ጎተ) አዲስና ደረጃውን የጠበቀ ቤተ መፃህፍት ከትላንት በስቲያ ምሽት ላይ አስረመቀ፡፡ ቤተ መፅሐፍቱ ሶስት የተለያዩ ክፍሎችን የያዘ ሲሆን አንደኛው መፅሐፍትን ለማንበብና በጥሞና ሀሳቦችን ለማውጠንጠን የተዘጋጀ ሲሆን ከ20 ሰዎች በላይ በአንድ ጊዜ ማስተናገድ ይችላል ተብሏል፡፡
2ኛው ክፍል ሲዲ፣ ኦዲዮ መፅሐፍት፣ ፊልም ማየት ለሚፈልጉና ኢንተርኔት መጠቀም ለሚፈልጉ ተጠቃሚዎች የተሰናዳ ክፍል ሲሆን አምስት አይፖዶችና ላፕቶፖችም የሚገኙበት እንደሆነና በአንዴ 18 ያህል ሰዎች የማስተናገድ አቅም ያለው ስለመሆኑ የቤተ - መፅሐፍትና የኢንፎርሜሽን ኃላፊው አቶ ዮናስ ታረቀኝ ተናግረዋል፡፡ ሶስተኛው ክፍል ደግሞ አነስተኛ ስቱዲዮና አረንጓዴ ስክሪን የተገጠመለት ክፍል ሲሆን ይህ ክፍል ስለፊልም በቡድን ለሚወያዩ፣ ፊልም ኤዲት ለሚያደርጉ፣ ስቱዲዮ ውስጥ ኢንተርቪው ለሚቀርፁና ለመሰል ተግባራት የሚያገለግል እንደሆነ የገለፁት አቶ ዮናስ በአጠቃላይ ቤተ - መፅሐፍቱ “መልቲ ፊንክሽናልና መልቲ ሚዲያ” ሆኖ ሙሉ አገልግሎት እንደሚሰጥ ተናግረዋል፡፡
በፊት የነበረውን የተለመደውን ቤተ - መፅሀፍት ለመቀየር ጥናት መስራቱንና ከውጭ የመጣች ባለሙያ የተለያዩ ተጠቃሚዎች የቋንቋ ተማሪችንና ሌሎችንም ከጎተ ጋር ግንኙነት ያላቸውን ተጠቃሚዎችን፣ ቃለ መጠይቅ ካደረገችና ፍላጎታቸው ከታወቀ በኋላ የቤተ መፅሐፍቱ ዲዛይን መስራቱን የገለፁት ኃላፊው ግንባታው አራት ወር እንደፈጀና ከ200 ሺህ ዩሮ በላይ እንደወጣበት ጨምረው ገልፀዋል፡፡ በምርቃት ስነ - ስርዓቱ ላይ ከንባብ ጋር የሚሰሩ ግለሰቦችና ድርጅቶች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና የባህል ማዕከሉ ኃላፊች ታድመው ነበር፡፡

በቅርቡ በመንግስት ውሳኔ ከእስር ከተለቀቁ የሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት አንዱ የሆኑት የኮሚቴው ህዝብ ግንኙነት የነበሩት ኡስታዝ አህመዲን ጀበል በሙስሊም መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ እንቅስቃሴዎች፣ ከመንግስት ጋር ስለተደረጉ ውይይቶች፣ ስለ እስር
ጊዜያቸው፣ ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ እንዲሁም ስለ ወደፊት ዕቅዳቸው ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርገዋል፡፡

ለእስር የተዳረጉበት አጋጣሚ ምን ይመስላል?
እኔ የተያዝኩት ሐምሌ 13 ቀን 2004 ነው። ዕለቱም የረመዳን የመጀመሪያ ቀን፣ እለተ አርብ ነበር፡፡ ከዚያ በፊት ባሉት ወራት፣ በተለይ ከየካቲት 26 ቀን 2004 በኋላ ከፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ጋር በህዝበ ሙስሊሙ ጥያቄዎች ዙሪያ ስድስት ሰዓት የፈጀ ውይይት አድርገን፣ በዚያ ላይ አለመግባባትና አለመስማማት ተፈጥሮ ነበር። ከዚያ በኋላ በመንግስት በኩል ኮሚቴውንም ጥያቄውንም በአሉታዊነት የመመልከትና “ህብረተሰቡን አይወክሉም፤ እስላማዊ መንግስት ሊመሰረቱ ነው” የሚሉ ቅስቀሳዎች በስፋት ይካሄዱ ነበሩ። በተለይ ከመጋቢት 7 ምሽት የኢቴቪ ፕሮግራም በኋላ ይሄ ቅስቀሳ ተጠናክሮ ነው የቀጠለው፡፡ የደህንነት ሃይሉም ከዚያ በኋላ፣ 24 ሰዓት ሙሉ እንቅስቃሴያችንን መከታተልና ስጋት መፍጠር ጀምሮ ነበር፡፡
ሚያዚያ 25 ደግሞ በሚዲያም 15 ደቂቃ የፈጀ ውንጀላ ያዘለ መግለጫ ተነቧል፡፡ እነዚህ ነገሮች ሲካሄዱ ቆይተው፣ የኮሚቴውን አባላት መያዝ የተጀመረው ሐምሌ 12 ቀን 2004 ነበር፡፡ እኔ የተያዝኩት ሐምሌ 13 ነው፡፡ ካራ ቆሬ አካባቢ በሚገኘው የጓደኛዬ ቤት እንዳለሁ ነው መጥተው የያዙኝ፡፡ ከያዙኝ በኋላ ፊቴን በጨርቅ ሸፍነው፣ በመኪና አድርገው ወደ ማላውቀው ቦታ ወሰዱኝ። በኋላ ላይ ነው ቴዎድሮስ አደባባይ በሚገኘው የደህንነት ቢሮ መሆኔን ያወቅሁት፡፡ ሌሎች ጓደኞቼ ያሉበትን እንድጠቁም ሲደበድቡኝና ሲያስፈራሩኝ ቆይተው፣ ሌሊት 6 ሰዓት ላይ ወደ ቢሮ አስገብተውኝ፣ ሽንት ቤት ገብቼ ፊቴን ሲፈቱኝ ነው ቸርችል ቪው ሆቴል የሚለውን አንፀባራቂ ማስታወቂያ አይቼ፣ ያለሁበትን ያወቅሁት፡፡ በማግስቱ ሐምሌ 14 ማዕከላዊ ወስደው አስረከቡኝ፤ ጠዋት 3 ሰዓት አካባቢ፡፡ ከአንድ ሰዓት ቆይታ በኋላ አራዳ ፍ/ቤት አቀረቡኝና የ28 ቀን ቀነ ቀጠሮ ጠየቁ። በወቅቱ ለፍ/ቤቱ የተናገሩት፤ ”ውጭ ሃገር ቆይቶ የአልቃይዳ አባል ሆኖ ሠልጥኖ መጥቷል፣ በሚሊዮን የሚቆጠር የገንዘብ ትራንዛክሽን በአካውንቱ ገብቷል፡፡ ህዝቡንም ለማሠልጠን እያደራጀ ነው፡፡ በዚህ ጉዳይ ስለምንጠረጥረው የ28 ቀን ቀጠሮ ይሰጠን” በማለት ነበር፡፡ በእውነቱ ስለ እኔ ሳይሆን ስለ ሌላ ሰው የሚናገሩ ነበር የመሰለኝ፡፡ በዚህ መልኩ የ28 ቀን ቀጠሮ ተፈቅዶ ወደ ማዕከላዊ ተመለስኩ፡፡
የሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ ከፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ጋር በወቅቱ ሲያደርጋቸው የነበሩ የውይይት ጭብጦች ምን ነበሩ?
17 አባላት ያሉት ኮሚቴ ነበር፡፡ ይሄ ኮሚቴ የሙስሊሙን ጥያቄዎች ያነገበ ነው፡፡ ከጥያቄዎቹ አንዱ፤ መጅሊስ የህዝበ ሙስሊሙ መሪ ድርጅት ቢሆንም በተግባር ደረጃ እንደ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ፍቃዱን በየ3 አመቱ የሚያድስ፣ የስራውን ሪፖርት የሚቆጣጠረውም የፍትህ ሚኒስቴር ነበር፤ በኋላ በ2003 መስከረም 24 ላይ የሃይማኖት ጉዳዮች ተጠሪነት ወደ ፌደራል ጉዳዮች እንዲዞር በፓርላማው ሲወሰን ፌደራል ጉዳዮች ተረክቧል፡፡ እኛ ደግሞ የመጅሊሱ አመራረጥ ግልፅ አይደለም፣ ማን ነው ሰዎቹን እየመረጠ ያለው? የሚሉ የህብረተሰቡን ጥያቄዎች ነው የያዝነው። ከዚያ ቀደም በ1992 በተመሣሣይ በመጅሊሱ ጉዳይ ጥያቄ ተነስቶ የተዳፈነበት ሁኔታ ነበር። በአንድ በኩል መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም የሚል መርህ ይቀመጣል፡፡ በሌላ በኩል፤ ለተቋማቱ አስተዳደር ፍቃድ እየሰጠ ያለው መንግስት ነው፤ ተቋሙ የስራ ሪፖርት የሚያደርገው ለመንግስት ነው፡፡ ይህ በሆነበት ሁኔታ መንግስት ከተቋሙ እጁን ያንሣ ሲባል፣ መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም የሚል ምላሽ ይሰጣል፡፡ በዚህ ጉዳይ ግልፅ የሆነ፣ የጠራ ነገር በሚወጣበት ሁኔታ ላይ ስንወያይ ነበር፡፡ በሁለተኛ ደረጃ፣ አህባሽ የሚባል አስተሳሰብ ከንቲባውን ጨምሮ በበርካታ የመንግስት ባለስልጣናት ድጋፍ አግኝቶ፣ አስተሳሰቡን ለማስፋፋት በርካታ ነገሮች ሲደረጉ ነበር፡፡ ለዚህ ደግሙ ሙሉ ማስረጃ ነበር፤ በዚህ ጉዳይም ላይ ስንነጋገር ነበር፡፡ እንደዚሁም የአወልያ ተቋም በቦርድ ይተዳደር የሚሉት ላይ ነበር ውይይታችን፡፡ መጀመሪያ ጥር 18 ቀን 2004 ኮሚቴው ከተመረጠ በኋላ ጥር 23 ቀን 2004 በወቅቱ የሲቪል ሠርቪስ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ጁነዲን ሣዶ “ኮሚቴውን ላነጋግር እፈልጋለሁ” ብለው እኔ ባልኖርበትም፣ ሌሎች አባላት ሄደው አነጋገሯቸው፡፡
በወቅቱ ካነጋገሯቸው በኋላ ዶ/ር ሽፈራውን ጨምሮ እንነጋገራለን በሚል በሌላ ጊዜ ቀጠሮ ተያዘ፡፡ የካቲት 5 ቀን 2004 ወደ ፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ሄድን፡፡ በወቅቱ ሚኒስትሩ አልነበሩም፤ ምክትሉ ነበሩ ፣ የአዲስ አበባ ፍትህ ቢሮ ሃላፊ አቶ ፀጋዬ ማሞና ከፖሊስ የተወከሉ ሰዎች ነበሩ፡፡ እነሱ ባሉበት ስለ ጉዳዩ ማብራሪያ ሰጠን፡፡ እነሱም “እንደ ኮሚቴ ወደኛ መምጣታችሁ ጥሩ ነው፤ ባለው ነገር ላይ ተነጋግረን መፍትሄ እንፈልጋለን” አሉን፡፡
መጀመሪያ ላይ የነበረው አዝማሚያ መጅሊስንም እኛንም አስቀምጠው ለማነጋገር ነበር። በወቅቱ እኛም አዝማሚያው ልክ አይደለም፤ እኛ ከመጅሊስ ጋር ተነጋግረን የምንጨርስ ቢሆኖ ኖሮ እናንተም ጋር መምጣት አያስፈልገንም ነበር፣ ህዝቡ መጅሊሱን አናውቀውም፤ አልወከልናቸውም እያለ ነው፤ ይባስ ብለው ከህዝቡ ፍላጎት ተቃራኒ እየሄዱ ስለሆነ እናንተ ለህዝቡ ያላችሁን ምላሽ ስጡን፤ አናናግራችሁም የምትሉ ከሆነም በግልፅ ንገሩን” ስንላቸው፣ መጅሊሱን ትተው እኛን ለማነጋገር ሞክሩ፡፡ በኋላ ላይ እኛ ከፌደራል ጉዳዮች ጋር መደበኛ ውይይት እያደረግን እያለ፣ መጅሊሱ “ህገወጥ ናቸው” ማለት ጀመረ፡፡ ከዚያም ወልቂጤን በመሣሠሉ አካባቢዎች የኮሚቴው አባላትን ማሠር ተጀመረ፡፡ በኋላ የካቲት 26 ቀን ባደረግነው ውይይት ላይ ሚኒስትሩም ተገኝተው ነበር፡፡ እኛም ውይይቱ በቴሌቪዥን ወይም በሬድዮ የቀጥታ ውይይት መደረግ አለበት የለበትም በሚል ነበር የተነጋገርነው፡፡ ይሄን ሀሣብ ያመጣንበት ምክንያት ደግሞ ሬድዮ ፋና ቀደም ብሎ እኔም የተሣተፍኩበት ውይይት አድርጎ ነበር፡፡ ያንን ውይይት ቆራርጠው እነሱ በሚፈልጉት መንገድ ስላቀረቡት፣ እንደ ኮሚቴ ተሰብስበን ማንኛውም ውይይት ወይ በቀጥታ መተላለፍ አልያም እኛም የምንቀዳበት ሁኔታ መኖር አለበት የሚል አቋም ይዘን ነበር፡፡ በዚህ ላይ ውይይት ካደረግን በኋላ “በቃ የውይይቱ ቅጂ ይሰጣችኋል” ተባልን፡፡
በዚሁ ወደ መደበኛ ውይይት ገብተን፣ ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ ውይይት እያደረግን ቆይተን፣ ከምሽቱ 1 ሰዓት አካባቢ እኛ ለሶላት ስንወጣ፣ እነሱ ወዲያው ለሬዲዮ ፋና መግለጫ ሰጡ። ከኮሚቴው ጋር ውይይት ተደርጎ፣ ለጥያቄዎች ምላሽ እንደተሰጠ አድርገው መግለጫ ሰጡ፡፡ እኛ ሰግደን ስንመለስ ሰው ቴክስት እያደረገ፣ “ምንድን ነው የተወሰነው?” በሚል ጥያቄ ነበር ያጣደፈን፡፡ እኛ ሶላት ላይ ስለነበርን የተባለውን አልሰማንም፡፡ መግለጫ እንደተሰጠም አላወቅንም ነበር፡፡ በወቅቱ በጣም ነው ያዘንነው፡፡ እንዴት የጋራ ድምዳሜ ላይ ሳንደርስ መግለጫ ይሰጣል? አልን፡፡ እነሱም “በቃ መንግስት በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፤ የመጅሊስ ምርጫም በኡላማ ምክር ቤት አማካኝነት ይካሄዳል፤ ጥያቄያችሁም ተመልሷል ከእንግዲህ ስብሠባ መደረግ የለበትም” አሉን፡፡ “አወልያን በተመለከተም ካስፈለገ ቦርድ ይቋቋማል፤ ቦርዱም ከፌደራል ጉዳዮች፣ ከማህበራዊ ማደራጃ ተደርጎ ሊዋቀር ይችላል” አሉን፡፡ በወቅቱ እኛ ጥያቄያችን እንዳልተመለሰ ስንነግራቸው፣ “ቢያንስ እንኳ የአወሊያ ጉዳይ እንዴት ተመልሶልናል ብላችሁ አትቀበሉም?” አሉን፡፡ በኋላ “በቃ ምላሻችሁን በፅሁፍ ስጡን፤ እኛ ለወከልነው ህዝበ ሙስሊም ደብዳቤውን ወስደን በንባብ እንነግራለን፤ በአፍ ግን ለህዝቡ ተናገሩ የምትሉትን አንቀበልም” አልናቸው፡፡ ከዚያም ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ለተለያዩ የመንግስት አካላት ደብዳቤዎችን ፃፍን። በመጨረሻ መጋቢት 14 በወቅቱ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ፅ/ቤት ሃላፊ የነበሩት አቶ ሬድዋን ሁሴን ያናግሯችሁ ተብለው አነጋገሩን፡፡ እሣቸውም፤ “መንግስት ጥያቄያችሁ ምላሽ ማግኘት አለበት ብሎ ያምናል፡፡ እኛ ከእናንተ የምንፈልገው በጉዳዩ ጊዜ ላይ ጊዜ አግኝተን ተነጋግረን ምላሽ እስክንሰጣችሁ ድረስ በአወሊያ የሚደረገው ነገር ለአንድ ወር እንዲቋረጥ ለህዝቡ እንድትነግሩልን ነው” አሉንና በዚሁ ተለያየን፡፡ በተቃራኒው በዚያ አንድ ወር ጊዜ ውስጥ ኮሚቴውን ማጥላላትና ኮሚቴው ላይ ተቃዋሚ ሰዎችን ለመፍጠር ነበር ጥረት ሲደረግ የነበረው፡፡ በኋላ አንድ ወሩ ሊገባደድ ሲል ሚያዚያ 11 ቀን 2004 የፀረ ሽብር ግብረ ሃይል አባላት የሆኑ 5 ሰዎች፣ የፖሊስ አዛዥና ሌሎች ጠርተው አነጋገሩን፡፡ በማግስቱ ሚያዚያ 12 ቀን በአወሊያ ረብሻ ለማስነሣት አላማ እንዳለ፣ ይሄን ስራ ማን እንደሚሠራ መረጃው ነበረን፤ ይሄን ጉዳይ ይዘን የተመረጥን ሰዎች ልናነጋግራቸው ስንሄድ እነሱ ጭራሽ “ከእንግዲህ ለሚፈጠር ችግር ሁሉ ሃላፊነቱን ትወስዳላችሁ” ወደሚል ማስፈራራትና ዛቻ ገቡ፡፡ በዚህ ጊዜ እኔ በግልፅ የተናገርኳቸው፤ “እኛ ምንም የመረበሽ አላማ እንደሌለን እናንተም ከኛ በላይ ታውቃላችሁ፤ ህዝቡም ያውቃል፤ ማንም ይሁን ማን ነገም ሆነ ከነገ በኋላ ረብሻ እንዳይኖር ለማድረግ እኛ ተዘጋጅተናል፤ ረብሻ ለመፍጠር ዝግጅት እንዳለም ጠንቅቀን እናውቃለን፤ እኛ እንዳይረበሽ ለማድረግ ሙሉ ዝግጅት አድርገናል” ስላቸው ተደናገጡና፤ “እንዴት መንግስትን በዚህ ትጠረጥራላችሁ?” አሉኝ፡፡ “እኛ ለሃገራችን ሠላም ለማስፈን እየሠራን ነው የምትሉት እውነት ከሆነ ጥሩ ነው፤ እኛ ያለን መረጃ ግን በተቃራኒው ነው” አልናቸው፡፡ በወቅቱ ተደናገጡ፡፡ በኋላ ውይይታችን ጨርሠን ስንወጣ፣ አነዋር መስጊድ ላይ የረብሻ ቅስቀሣ ወረቀት ተበተነ። እኛም አወሊያ ት/ቤት ጀርባ ባለ ጫካ የፀጥታ አካላት ተደብቀው እንዳለ መረጃ ነበረን፡፡ ይሄ መረጃ በማህበራዊ ሚዲያም እንዲወጣ አደረግን፡፡
ሚያዝያ 12 ቀን መድረክ መሪው ኡስታዝ ሣቤር ይርጉ ነበር፡፡ እሱም “እንኳን በሠላም መጣችሁ፤ ጫካ ውስጥ ያላችሁትን ጨምሮ” በማለት ህዝቡ ጫካ ውስጥ እንዳሉ እንዲያውቅ አደረገ፡፡ በዚህ መልኩ በእለቱ ተደግሶ የነበረው ረብሻ ሳይፈጠር ቀረ፡፡ በኋላ በተለያዩ የመንግስት ባለስልጣናት ኮሚቴውን ማጉላላት፣ መፈረጅ ተጠናክሮ ቀጠለ፡፡ ህዝብና ኮሚቴውን የመነጣጠል ሙከራዎች ቀጠሉ፡፡ በዚህ ሁኔታ ቀጥለን ሐምሌ 4 ቀን እኔና አቡበከር አለሙን ያዙን፤ አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ወስደው ለ4 ሰዓት ካሰሩን በኋላ፤ “ከአሁን በኋላ የመጅሊስ ጉዳይ፣ የሙስሊም ጥያቄ የምትሉትን ነገር የማታቆሙ ከሆነ በህይወታችሁ ፍረዱ” ብለው አስፈራርተው ለቀቁን፤ “የመጨረሻ ማስጠንቀቂያ ነው የሰጠናችሁ” አሉን፡፡
ሐምሌ 6 ምሽት ለሐምሌ 8 የሠደቃ ፕሮግራም አወሊያ ላይ የተዘጋጀ ዝግጅት ነበር። 40 ያህል በሬዎች ነበሩ፤ የታረደውን ስጋም ያልታረዱትን በሬዎችም ወስደው በርካታ ሰዎችን አሰሩ፡፡ ሐምሌ 7 አነዋር መስጊድ ሄጄ፣ ሰውን ለማረጋጋት፣ እኛ የያዝነው መንገድ ሠላማዊ ነው በሚል ንግግር አደረግሁ፡፡ የዚህን ቪድዮም ኢንተርኔት ላይ ዛሬም ማንኛውም ሠው መመልከት ይችላል። በማግስቱ ሐምሌ 8 ቀን እኔ፣ አቡበከር፣ ካሚል ሸምሱ፣ አህመድ ሙስጠፋ ወደ አወሊያ ስንሄድ መንገድ ላይ አንዲት ነጭ ኒሳን መኪና ከፊታችን ቀድማ መንገድ ዘጋችብን፡፡ ከዚያም ሌሎች መኪኖች ከኋላችን መጥተው ሰዎች ወርደው፤ “እንንቀሳቀሳለን ብትሉ ግንባራችሁ ነው የምንለው” ብለው ሽጉጥ ደቅነውብን፣ ነጯን መኪና እንድንከተል አዘዙን፡፡ “እናንተ እነማን ናችሁ? መታወቂያ አሣዩን” ስንላቸው፣ “ለእናንተ አይነት ሰዎች ነው መታወቂያ የምናሣየው” ብለው እኔን በቦክስ መቱኝ፤ በዚህ መልኩ አጅበውን ይዘውን ሄዱ፡፡ ልክ ሱማሌ ተራ ስንደርስ፤ “እነዚህ ሰዎች ህገ ወጦች ናቸው፤ መታወቂያም ሊያሣዩን አልፈለጉም ዝም ብለን መከተል የለብንም፤ ከቻልክ አምልጥ አልነው” ሹፌራችንን፤ ሹፌራችንም እንደ ምንም ብሎ አመለጣቸው፡፡ ከዚያም አንዋር መስጊድ ገባን፤ ፕሮግራሙም ተካሄደ፡፡ ከዚያ በኋላ 8 ሰዓት ላይ ሁላችንም የኮሚቴው አባላት ተሰብስበን አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ሄደን “ትፈልጉናላችሁ ወይ?” አልናቸው፡፡ እነሡም፤ ”እኛ የምናውቀው ነገር የለም፣ አንፈልጋችሁም” አሉን፡፡ ከዚያ በኋላ የደህንነት ክትትል በዙሪያችን ይደረግ እንደነበር እናውቅ ነበር፡፡ በአራተኛው ቀን ሐምሌ 12 ቀን ጀምሮ አባላቱን ማሰር ጀመሩ ማለት ነው፡፡
መንግስት መጀመሪያ ላይ እውቅና ሰጥቷችሁ ሲያነጋግራችሁ ከቆየ በኋላ እንዴት ወደ ህገ ወጥነት ቀየራችሁ? ምክንያቱን ለመረዳት ሞክራችሁ ነበር?
ከታሠርን በኋላ የደህንነት አመራር ከነበረው ወልደስላሴ ጋር በእስር ቤት ተነጋግረን ነበር፡፡ እሱ የነገረኝ በወቅቱ መንግስት በማስፈራራትም በሌላም መንገድ እኛን ወደሚፈልገው ለመጠምዘዝ ሲሞክር ነበር፡፡ ይሄ ሃሳቡ ሊሣካለት አልቻለም፡፡ እንዳጋጣሚ ደግሞ እኛ መሀል ለኢህአዴግም ቅርብ የሆኑ ሰዎች ነበሩ፡፡ እነሱ በቀላሉ ይመለሣሉ ተብሎ ተጠብቆ ነበር፤ ለማግባባትም ሙከራ ተደርጎ ነበር። እኛ ግን አስቀድመን ይሄ ሊመጣ እንደሚችል ገምተን እንቅስቃሴያችን በጥንቃቄና ግልፅነት በተሞላበት መልኩ እያካሄድን ስለነበር ለመከፋፈል አጀንዳው አልተመቸነውም፡፡ አንዴ በብሄር፣ አንዴ በፖለቲካ፣ አንዴ በእድሜ ለመከፋፈል ብዙ ሙከራ ተደርጓል፡፡ ይሄ በኮሚቴው አባላት ፅናት ሊሣካ አልቻለም፡፡ ይሄ አልሣካ ሲል ህብረተሰቡ ጥያቄው ትክክል እንደሆነ፣ ኮሚቴው ግን ሌላ አላማ እንዳለው በግልፅ ወደ ማጥላላት ነው የተገባው፡፡ ይሄን ከወልደስላሴ ጋር በማረሚያ ቤት ካደረግነው ውይይት መረዳት ችያለሁ፡፡ በወቅቱ እስከ መጨረሻ የዘለቀው የኛ ግልፅ አቋም፤ “ለህዝቡ ያላችሁን ምላሽ በደብዳቤ ስጡን ወይም ከእናንተ የተወከለ ህዝቡ በተሰበሰበበት ተገኝቶ ያስረዳ” የሚል ነበር፡፡
የፍርድ ቤት ጉዳያችሁና የህዝቡ እንቅስቃሴስ ምን ይመስል ነበር?
እኛ የግል ጥያቄ ሳይሆን የህብረተሰቡን ጥያቄ ነበር የያዝነው፡፡ እኛም ከታሰርን በኋላ በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ህዝበ ሙስሊም ጥያቄውን ይዞ ሲቃወም ነበር፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ ታስረዋል። ይሄ እስር ቤት ሆነን ያሳየን የነበረው፣ መንግስት ከህዝቡ ጥያቄ በተቃራኒ መቆሙን ነው፡፡
ህብረተሰቡ እኛ ያለመክዳታችንን አውቆ በዚያ መልኩ መንቀሳቀሱ ለሁሉም በግልፅ የታየ ነው። እኛ በማረሚያ ቤት ሆነን ይጎበኘን የነበረው በሺዎች የሚቆጠር ህዝብ ነው፡፡ አስታውሳለሁ፤ አንድ ቀን የመጡ ጠያቂዎች መቶም ሃምሣ ብርም እየሰጡኝ ነበር የሚሄዱት፤ በመጨረሻ የሠጡኝን ገንዘብ ስቆጥረው 17 ሺህ ብር ነበር የሆነው፡፡ በኋላ ያንን ገንዘብ “እኔ አልፈልግም፤ ይሄ ሁሉ ህዝብ መጥቶ የጠየቀኝ የያዘኩትን አላማ ስለሚደግፍ ነው” በሚል ለማረሚያ ቤቱ ሃላፊዎች፣ ለማረሚያ ቤቱ የውሃ ችግር ማቃለያ ታንከር ይገዛ ዘንድ ብሰጥም ሃላፊዎቹ፤ “ለመቀበል ፍቃደኛ አይደለንም” ብለው ችግር የፈጠሩበትን ሁኔታ አስታውሣለሁ፡፡ በኛ የክስ ሂደት ምስክር ለመሆን በሺዎች የሚቆጠሩ ናቸው በራሳቸው ፍቃድ የተመዘገቡት፡፡ የቀረበብን ክስም ግልፅ ነበር፡፡ አንደኛው፤ የኮሚቴው አባል መሆናችን ብቻ እንደ ሽብር ነው የተቆጠረው፣ ሌላው ቅስቀሣ ማድረግ የሚል ነው፡፡ ስለዚህ ህዝብ ፊት የቀረቡ ንግግሮች ናቸው ያስከሰሱን፡፡ ስለዚህ ህዝቡ ለምስክርነት ለመቆም አልከበደውም። በአካባቢው የነበሩ ክርስቲያኖች ሳይቀሩ ነው የመከላከያ ምስክር ሆነው የቀረቡልኝ፡፡ ይሄ ሁሉ ማስረጃ ቀርቦ ባለበት ነው ፍ/ቤቱ ጥፋተኛ ነህ ያለኝ፡፡ ህብረተሰቡም በዚያ መንገድ ሲንቀሳቀስ የነበረው አለኝታነቱን ለመግለፅ ነበር፡፡
በማረሚያ ቤት ታመው እንደነበር በማህበራዊ ሚዲያም ተገልፆ፣ ህክምና እንዲያገኙ ቅስቀሳ ሲካሄድ ነበር፤ ህመምዎ ምን ነበር? አሁንስ የጤንነትዎ ሁኔታ?
እኔ ወደ ማረሚያ ቤት የወረድኩት ጥቅምት 19 ቀን 2005 ነው፡፡ ክስ የተመሠረተብኝ ቀን ማለት ነው፡፡ ከዚያ በፊት ማዕከላዊ ለ3 ወር ያህል ቆይቻለሁ፡፡ በጨለማ ቤት ታስሬያለሁ፤ የተለያዩ ማንገላታቶች ተፈፅመውብኛል። ቃሊቲ ማረሚያ ቤት ከገባሁ በኋላ ብዙ ክትትል ይካሄድብኝ ነበር። ቤተሠብ እንዳይጠይቀንም እንከለከል ነበር። ውስን የቤተሰብ አባላት ብቻ ነበሩ እንዲጠይቁን የሚደረገው፡፡ እኛን በተለየ መልኩ የመመልከት ሁኔታዎች ነበሩ፡፡ የኩላሊት ህመም በፀና ያመመኝ በመጋቢት 2009 ነበር፡፡ እዚያው ክሊኒክ ስሄድ ኢንፌክሽን ነው ተብዬ መድሃኒት ተሠጠኝ፤ ግን ብዙም አልተሻለኝም ነበር፡፡ በኋላ ወደ ውጪ ወጥቼም እንድታከም ስጠይቅ ነበር፡፡ በዚህ ሁኔታ ከቆየሁ በኋላ ነሐሴ 5 ቀን ነው ከማረሚያ ውጪ ህክምና ያደረግሁት። በወቅቱ ኩላሊትህ ውሃ ይዟል ነው የተባልኩት፡፡ ሪፈር ወደ ጳውሎስ ሆስፒታል ብባልም ያንን ተከልክያለሁ። ለ1 ወር ያህል ህክምና ማግኘት ሳልችል በህመም ስሰቃይ ነበር፡፡ ለነሐሴ 17 የተፃፈው ሪፈር መስከረም መጨረሻ አካባቢ ነው በብዙ ውጣ ውረድ ወደ ጳውሎስ የሄድኩት። ከዚያ በኋላ ነው ፌስቡክ ላይ ጉዳዬ የተነገረው። በወቅቱ እኔ በማህበራዊ ሚዲያ እንደወጣሁ አላወቅሁም ነበር፡፡ በኋላ የማረሚያ ቤቱ የክሊኒክ ሃላፊ ጠርታኝ፤ “ምን በድለንህ ነው በማህበራዊ ሚዲያ ህክምና ተከለከልኩ” ያልከው አለችኝ፡፡ እኔ በወቅቱ ምንም አላውቅም ነበር፡፡ ይሄን አስረዳኋት፤ እሷም “በቃ ማንኛውም ችግር ካለ ለኔ ንገረኝ” ብላ ስታግባባኝ ነበር። በኋላም ወደ ህክምና ስወሰድ ፎቶ ግራፍ እንዳልነሣ በጥንቃቄ ነበር፡፡ በማያሣይ መስታወት መኪና ውስጥ ተደርጌ ነበር ወደ ህክምና የምወሠደው፡፡ ህመሜ የሽንት ፊኛ ቱቦ መጥበብ የፈጠረው በመሆኑ ቱቦ ተገጥሞልኝ ነበር ለ1 ወር የቆየሁት፤ ለሶስት ለአራት ቀናት ሽንት ቤት መቀመጥ አልችልም ነበር፤ ደም ነበር የምሸናው፡፡ አሁን የተባለው ውሃ ወጥቷል፣ ቱቦውም ወጥቷል፡፡ ጤንነቴም እየተመለሰ ነው፡፡
ከእናንተ ጋር የአቶ ጁነዲን ሣዶ ባለቤትም ታስረው ነበር፤ ከእናንተ ጋር የነበራቸው ግንኙነት ምን ነበር?
ወ/ሮ ሃቢባ መሃመድ ትባላለች፡፡ ማዕከላዊ ነው ለመጀመሪያ ጊዜ የጁነዲን ሣዶ ባለቤት ተብላ ያየኋት እንጂ በስምም በአካልም ትውውቅ አልነበረንም፡፡ እሷ ላይ በነበረው ክስ፣ ምስክር ተብለው የመጡት ሹፌሯና አጃቢዎቿ ናቸው፡፡ የአቶ ጁነዲን እናት፤ “መስጊድ በቦታዬ ላይ ይሠራ” የሚል ኑዛዜ ማስቀመጣቸውን ተከትሎ፣ ያንን መስጊድ ለማሠራት ከሚደረግ ጥረት ጋር ተያይዞ እንደታሠሩ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ ከእኛ ጋር ግን በወቅቱ አንተዋወቅም ነበር፡፡
ከሃይማኖት መምህርነትዎ ባሻገር የታሪክ ምሁርም እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ የሚፅፏቸው የታሪክ መጻህፍት ነባሩን የኢትዮጵያ የታሪክ መረዳት የሚያፈርስ ነው የሚል ትችት ይቀርብባቸዋል? በዚህ ላይ እርስዎ ምን ይላሉ?
እንግዲህ እኛ የኢትዮጵያ ታሪክ ስንል መሆን ያለበት የኢትዮጵያን ሁሉ ታሪክ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ታሪክ ብለን የአንደኛውን ህዝብ፣ ሃይማኖት ወይም አካባቢ፣ ወይም ስልጣን ላይ ያለው አካል ታሪንክን የምናወራ ከሆነ ስህተት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ታሪክ ካልን አሸናፊውም ተሸናፊውም የየራሱ ትርክት አለው፡፡ ይሄ እውቅና ሊያገኝ ይገባዋል፡፡ ታሪክ የሚፃፈው በአሸናፊው እንደሆነ ይታወቃል፤ ነገር ግን የተሸናፊውስ ታሪክ? ብለን መጠየቅ አለብን። የኢትዮጵያን ታሪክ ሙሉ ሊያደርግ የሚችለው የአሸናፊውንም የተሸናፊውንም ታሪክ አሟልቶ ማቅረብ ሲቻል ነው፡፡ እስከ ዛሬ ስንሠማው፣ ስንማረው የነበረው ታሪክ የሁሉንም ብሄሮች ይወክላል ወይ? የሁሉንም ሃይማኖት ይወክላል ወይ? ብለን በንፁህ ህሊና መጠየቅ አለብን፡፡ እስከ ዛሬ በትምህርት ስርአቱ ተካትቶ የተማርናቸው ታሪኮች የነገስታቱን ነው፡፡ በወቅቱ የነበሩ ነገስታትን ፍላጎት መሠረት አድርገው ነው የተቀረጹት። ዛሬም በትምህርት የሚቀርበው ታሪክ የመንግስትን ፍላጎት ተከትሎ ነው፡፡ ለምሳሌ የሙስሊሙ ታሪክ ምን ነበር? የሚለው በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ እንዴት ነው የቀረበው የሚለውን ማየት አለብን፡፡
እርስዎ የሚጠቀሟቸው የታሪክ ማጣቀሻዎች ምንድን ናቸው?
ታሪክ የጋራ መግባባትን በሚፈጥር መሠረት ላይ ካልቆመ መልካም አይደለም፡፡ የኔ ማጣቀሻዎች ትኩረት ሳይሠጣቸው የነበሩ ነገር ግን በትምህርት ስርአቱ ውስጥ የነበሩ መፅሐፍት፣ ሁለተኛ የሙስሊም ምሁራን በአረብኛና በተለያዩ ቋንቋዎች በየዘመናቸው የፃፏቸውን ማኑስክሪፕቶች፣ በእድሜ የገፉ ሽማግሌዎችንና የተለያዩ ምንጮችን በመጥቀስ ነው፡፡ ይሄንንም በግልፅ በመፅሐፎቼ አመላክቻለሁ፡፡ ሁሉም ያለውን ማስረጃ አምጥቶ መሃል ላይ የሚያግባባን ታሪክ ተቀምጦ በትምህርት ስርአቱ ውስጥ ተካትቶ ልጆቻችን ካልተማሩ ለወደፊት አስቸጋሪ ሊሆን ይችላል፡፡ ዛሬ ላይ አብዛኞቹ አለመግባባቶች ያሉት ስለ ትናንት እንጂ ስለ ዛሬ አይደለም፡፡ ይሄ መታረቅ አለበት፡፡ ትናንት ምን ሆኖ ነው ዛሬ ላይ የደረስነው የሚለውን መፈተሽና ወደ ጋራ መግባባት መምጣት አለብን። በታሪክ ላይ የጋራ መግባባት መፍጠር ለነጋችን መልካም ይሆናል፡፡
ከዚህ በኋላ ምን ለመስራት አቅደዋል?
እኔ እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ፤ ኢትዮጵያን ይጠቅማል ባልኩት ነገር ሁሉ እሳተፋለሁ፡፡ ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ ማንንም የሰው ልጅ ይጠቅማል ባልኩት ሁሉ ከመሣተፍ ጎን ለጎን እንደ ሙስሊም ከሃይማኖት ጋር በተያያዘ እሣተፋለሁ። በብሄርም ጉዳይ እንደ አንድ የኦሮሞ ብሄር ተወላጅ፣ አስፈላጊውን ተሳትፎ አደርጋለሁ፡፡
እስከ ዛሬ በሙስሊምና እስልምና መንገድ ብቻ መታጠሬ ቀርቶ በሃገሬ ጉዳይ በማንኛውም መልኩ ከሌሎች ወገኖቼ ጋር የተሻለች ኢትዮጵያን ለመፍጠር እንዲሁም ሙስሊሙ ማህበረሰብ የነቃ ተሳትፎ እንዲያደርግ ጠንክሬ እሠራለሁ፡፡

 

ለ 5 ዓመታት ተቋርጦ ቆይቷል

የሕንፃ ግንባታው ለአምስት ዓመታት ተቋርጦ የቆየው የርእሰ አድባራት ወገዳማት አኵስም ጽዮን ማርያም ቤተ መዘክር ግንባታ ለማስጀመር፣ የ160 ሚሊዮን ብር አዲስ ውል ተፈረመ፡፡
ጨረታውን በአዲስ መልክ በማውጣት፣ ባለፈው የካቲት 12 ቀን የግንባታ ኮሚቴው ዋና ሰብሳቢ ብፁዕ አቡነ ገሪማ እና አሸናፊ የሆነው ተቋራጭ ድርጅት የስምምነት ውል ሰነድ ተፈራርመዋል፡፡
ከድርጅቱ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ ኢንጅነር ተክለ ሃይማኖት አስገዶም ጋር በመንበረ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት አዳራሽ በተከናወነው የፊርማ ሥነ ሥርዐት ላይ የተገኙት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፣ “የቀድሞው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ፣ እግዚአብሔርንና ቤተ ክርስቲያንን በመተማመን ያስጀመሩት ይህ ታሪካዊ ቤተ መዛግብት፣ የኢትዮጵያውያን ሀብትና ንብረት ነው፤” ብለዋል፤ ለፍጻሜውም ሁሉም ኢትዮጵያዊ በተለይም የቤተ ክርስቲያን አካላት እያንዳንዳቸው ትብብርና ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪያቸውን አስተላለፈዋል፡፡
ቤተ መዘክሩን ለማጠናቀቅ 160 ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅና በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ ሊጠናቀቅ እንደሚችል ተገልጿል፡፡
የርእሰ አድባራት ወገዳማት አኵስም ጽዮን ሙዚየም ግንባታ፣ በሚያዝያ ወር 2003 ዓ.ም. በቤተ ክርስቲያኒቱ ቋሚ ሲኖዶስ ተወስኖ በቀድሞው ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ይፋ የተደረገ ቢኾንም፤ እስከዛሬ የግንባታው ሒደትና ወጪ አነጋጋሪ ሆኖ መዝለቁ ታውቋል፡፡
በአንድ ወቅት የቤተ ክርስቲያኒቱ ልሳን የሆነው “ዜና ቤተ ክርስቲያን” ጋዜጣ፣ “ለግንባታው ፕሮጀክት በውጭ ምንዛሬ 8.9 ሚሊዮን ዮሮ እና 25 ሚሊዮን ዶላር፣ በኢትዮጵያ ገንዘብ ደግሞ ከ200 ሚሊዮን እና ከ400 ሚሊዮን ብር በላይ” ወጪዎች እንደሚያስፈልጉ የጠቀሰ ሲሆን፣ የወጪው መጠን መለያየት በፕሮጀክቱ ላይ ጥያቄዎችና ጥርጣሬዎች ሲያስነሣ ቆይቷል፡፡
ከአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት ለሙዚየሙ ግንባታ ርዳታ ለማሰባሰብ፣ በኅዳር ወር 2004 ዓ.ም. የተቋቋመው አስተባባሪ ኮሚቴ ላለፉት 6 ዓመታት በሥራ ላይ የቆየ ቢሆንም፤ በሙዳየ ምጽዋት የታቀደውን ያህል ገንዘብ በወቅቱ ማግኘት እንዳልቻለ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡
እስከ አሁንም የተሰበሰበው ገንዘብ ከ25 ሚሊዮን ብር ያልበጠ እንደኾነ የጠቆሙት ምንጮች፤ መሠረቱ ወጥቶ የቆመው ግንባታ ከተቋረጠም አምስት ዓመት ማስቆጠሩን ጠቁመዋል፡፡ “ፀሐይና ዝናብ እየተፈራረቁበት ብረቱ እየዛገ፣ ብሎኬቱ እየፈራረሰ ነው፣” ይላሉ ምንጮቹ፡፡
በሌላ በኩል ዩኔስኮ፣ “የሙዚየሙ ሕንፃ ዲዛይን መካነ ቅርሱን የሚሸፍን መኾን የለበትም፤” በሚል ማሻሻያ እንዲደረግበትና ግንባታውን ለማጠናቀቅ ጥቅም ላይ የሚውሉ ቁሳቁሶችም ከመካነ ቅርሱ (ሐውልቱና የጥንቱ ቤተ ክርስቲያን) መልኮች ጋር እንዲጣጣሙ ማሳሰቡን ምንጮቹ አክለዋል፡፡
በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣንና በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ትብብር፣ የዲዛይኑ ማሻሻያ ተደርጎ ለዩኔስኮ ከተገለጸና ከተፈቀደ በኋላ ጨረታው ወጥቶ የግንባታው ውል እንደ አዲስ መፈረሙን አስረድተዋል፡፡ ከአዲስ አበባ አብያተ ክርስቲያናት የገንዘብ አስተዋፅኦውን የሚያስተባብረው ኮሚቴም በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ እንደ አዲስ ተዋቅሮ በሥራ አስኪያጅ እንዲመራ የተደረገ ሲኾን፣ በሙዳየ ምጽዋት የሚሰበሰበው ርዳታም እንደ አድባራቱ የገቢ አቅም ወደ “ቁርጥ መዋጮ” መዞሩ ታውቋል፡፡
የ“ቁርጥ መዋጮው” ድልድል፣ በአድባራት በቂ ውይይት አልተካሔደበትም፤ ያሉት ምንጮቹ፣ ይህም የተፈለገው አስተዋፅኦ እንዳይገኝ ዕንቅፋት እንዳይሆን ስጋታቸው ገልጸዋል፤ የአድባራቱን አስተዳደር የማሳመን ተጨማሪ ሥራ እንደሚያስፈልግና ቀድሞውንም በቂ ገንዘብ ሳይያዝ በተለጠጠ በጀት ግንባታውን መጀመሩ አግባብነት የሌለው በመሆኑ ለቁጥጥርም ስለሚያዳግት ሊታረም ይገባል፤ ብለዋል፡፡