Administrator

Administrator

በሀገራዊ ምርጫ ውጤት የክልልና የፌደራል መንግስታት ስልጣን በተለያዩ የፖለቲካ ሃይሎች ቢያዝ፣ በሁለቱ መንግስታት መካከል የሚኖረውን ግንኙነት የሚደነግግ የህግና ፖሊሲ ማዕቀፍ መዘጋጀቱ ተገለፀ፡፡
የህግ ማዕቀፍ ዝግጅቱ 4 አመታትን መፍጀቱ የተገለፀ ሲሆን ሀሳቡ በፌደራልና አርብቶ አደር ጉዳዮች ሚ/ር እና በፌዴሬሽን ም/ቤት ፈልቆ የተዘጋጀ ነው ተብሏል የፖሊሲ የህግ ማዕቀፉ ከዚህ ቀደም በፌደራል መንግስቱና በክልል መንግስታት መካከል የነበረውን ተለምዷዊ የመንግስታት ግንኙነት በህግ የሚያጠናክር ይሆናል ተብሏል፡፡
እስካሁን የነበረው የፌደራልና የክልል መንግስታት ግንኑነት፤ መደበኛ ያልነበረ ሲሆን አሁን የሚዘጋጀው የፖሊሲ የህግ ማዕቀፍ፣ ህገ መንግስቱን መሰረት አድርጎ በህግና በፖሊሲ የተደገፈ ዘላቂነት ያለው መደበኛ ግንኙነት እንዲኖር የሚያደርግ መሆኑን በፌዴሬሽን ም/ቤት የዲሞክራሲያዊ አንድነት የመንግስታት እርስ በእርስ ግንኙነት ማጠናከሪያ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አስቻለው ተክሌ ለአዲስ አድማስ አብራርተዋል፡፡
በህገ መንግስቱ አንቀፅ 51፤ የፌደራል መንግስቱ የሃገሪቱን የኢኮኖሚ ማህበራዊና ልማት ስትራቴጂ የማውጣትና የማስፈፀም ስልጣን እንዳለው የሚደነግግ ሲሆን አንቀፅ 52 ደግሞ የክልል መንግስት የራሳቸውን የኢኮኖሚ፣ማህበራዊና የልማት እቅድ የማውጣት ስልጣን እንዳላቸው ይደነግጋል፡፡
እነዚህን ተግባራት እስካሁን የፌደራልና የክልል መንግስታት ተለምዶአዊ በሆነ መንገድ በምክክር ሲሰሩ ቢቆዩም ህገ መንግስታዊ ድንጋጌያቸውን በዝርዝር የሚያብራራ የህግ ማዕቀፍ በማስፈለጉ ላለፉት አራት አመታት ይኸው ጥናትና ዝግጅት ሲካሄድ መቆየቱ ተገልጿል፡፡
በህንድ ለረዥም አመታት ኮንሰርቫቲቭ ፓርቲ የፌደራሉንም የክልል መንግስቱንም ስልጣን በብቸኝነት ተቆጣጥሮ መቀጠሉንና ኋላ ላይ በክልል ያለው ስልጣኑ በተቃዋሚዎች እየተሸረሸረ መጥቶ የፌደራል መንግስትነት ቦታውንም ማጣቱን በተሞክሮነት የጠቀሱት አቶ አስቻለው፡፡ በኛም ሀገር የምርጫ 97 አጋጣሚ ማሳያ በመሆኑ፣ ለወደፊት የተለያዩ ፓርቲዎች ወደ ስልጣን ቢመጡ ሀገሪቱ ጤናማ በሆነ መልኩ እንድትቀጥል አርቆ በማሰብ የተዘጋጀ የፖሊሲ የህግ ማዕቀፍ መሆኑን ለአዲስ አድማስ አብራርተዋል፡፡ እንደየዘመኑ አዳዲስ ጉዳዮች ሲፈጠሩ የሚስተናገዱበትን መንገድም የፖሊሲ ህግ ማዕቀፉ አስቀምጧል ብለዋል አቶ አስቻለው፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን የዱር አራዊቶች ሁሉ በአንድነት ተሰብስበው አውጫጪኝ ያደርጋሉ፡፡ የጫካው ንጉስ አያ አንበሦ ናቸው ሰብሳቢው፡፡
የስብሰባውን አላማ እንዲህ ሲሉ ገለፁ፡-
“የስብሰባችን አላማ በየጊዜው በአደን የመጣ ንብረት ይጠፋል፡፡ ዋሻ፣ ቁጥቋጦ፣ ዛፍና የመሳሰሉት ማደሪያና መኖሪያዎቻችን የአንዱን አንዱ

እየወሰደ፣ ጉልበተኛው ደካማውን እየቀማ ስላስቸገረ፤ እነዚህን ለማስተካከል ነው” አሉና “የተወሰደ ንብረት በሙሉ ለባለቤቶቹ ይመለሳል”

ሲሉ ደመደሙ።
በዚህ መካከል ጦጢት እጇን አውጥታ፤ “እኔ ከጫካው ውስጥ ማደሪያዬ የሆነው ዛፍ ጠፍቶብኛልና ሊመለስልኝ ይገባል” አለች፡፡
ይሄኔ ዝንጀሮ እጁን አወጣና፤
“እኔ ጦጢትን እቃወማለሁ፡፡ ተቃውሞዬም ጦጢት በየጊዜው ከአንድ ዛፍ አንድ ዛፍ ስለምትዘል የተወሰነ ዛፍ የላትም” አለ፡፡
ጦጢት መልሳ ዝንጀሮን ተቃወመች፤
“አያ አንበሶ፣ የእኔ ዛፍ የተለየ ነው፡፡ ምክንያቱም ቅርንጫፎቹን ማር ቀብቻቸዋለሁ፡፡”
አያ ነብሮ እዚህ ላይ ጣልቃ ገባና፤
“ጦጢት ማሩን ከየት እንዳመጣች እንድትጠየቅልኝ እፈልጋለሁ!” አለ፡፡
ጦጢትም፤
“እጫካ ውስጥ የተሰቀለ ቀፎ አግኝቼ፤ ከዚያ ቆርጬ ነው!” አለች፡፡
ጦጢት ይሄን እያስረዳች ሳለች እነ ቀበሮ፣ እነ ተኩላ፣ እነ ዝንጀሮ የጦጢትን ማር ሊልሱ፣ ከምኔው ሄዱ ሳይባል ወደ ዛፉ ሄደዋል፡፡
ይሄኔ ጦጢት፤
“በቃ በቃ ዛፉ የት እንዳለ አውቄያለሁ” አለች፡፡
“እንዴት አወቅሽ?” አለ አያ አንበሶ፤ ለምን በስብሰባችን ትቀልጃለሽ በሚል የቁጣ ስሜት፡፡
“አያ አንበሶ፤ እነ ዝንጀሮ ወዴት እንደሄዱ ይጣራልኝ፡፡ አሁን እዚህ የነበሩት የት ተወሰሩ?”
ዕውነትም አያ አንበሶና አያ ነብሮ ዞር ብለው ቢያዩ፤ እነ ዝንጀሮ የሉም፡፡ ስለዚህ ነብር ወደ ጫካ ተላከ፡፡ ጦጢት ተከትላ ካልሄድኩ አለችና

አስቸገረች፡፡
አያ አንበሶ፤
“ያንቺን ጉዳይ እያጣራን አንቺ ወዴት ትሄጃለሽ?” አላት፡፡
ጦጢትም፤
“በእነ ዝንጀሮ ጅልነት ልስቅባቸው ነው የምሄደው”
“እንዴት?”
‹‹እኔ የዛፉን ቅርንጫፎች ምንም ማር አልቀባሁም፡፡ እነሱም ግን ዛፉን ስለሚያውቁት ወደዚያው ሂደዋል፡፡ ማሩ የለም! አሁን ማ ሌባ እንደሆነ

አወቅን … አያ አንበሶ!” አለች እየሳቀች፡፡
*   *   *
ማር መላስ የማይፈልግ የለም፡፡ ያም ሆኖ ግን አንዱ አንዱን እየጠለፈ፣ አንዱ የአንዱን እየዘረፈ ወይም ከመንግስት እየመዘበረ፣ የሚኖርበትን

ሥርዓት ማስወገድ ተገቢ ነው፡፡ እጅግ የተወሳሰበና የተቆላለፈው የሙስና መረብ፣ በተለይ ከፖለቲካው ጋር ሲተበተብ ለያዥ ለገራዥ

ማስቸገሩን እያየነው ነው!! የሙስናን አሻጥር ለመረዳት በተለይ ዛሬ ዓይንን ማሸት አይፈልግም፡፡ ምን ያህል የሀገርና የህዝብ ገንዘብ ለግል ጥቅም

እየዋለ መሆኑን፣ የተጠረጠሩ የሙስና ባለ እጆችን ማስተዋል ብቻ በቂ ነው፡፡ ሆን ተብሎም ሆነ ለጥንቃቄ ተብሎ አሊያም በስህተት የሙስና

ክስ ዘግይቷል ብንል ማጋነን አይሆንም፡፡ አሁንም መፍጠን አለበት፡፡ የሙስና ዘዴው በአብዛኛው የሚታወቅ ነው፡፡ በዘመኑ ቋንቋ የተበላ ዕቁብ

ነው
‹‹እኔም ሌባ፣ አንተም ሌባ
ምን ያጣላናል፤ በሰው ገለባ!››
የሚባልበት ያፈጠጠ፣ ያገጠጠ ጊዜ ነው፡፡ አለቃና ምንዝር ሳንለይ የሚሠርቁ እጆች መያዝ አለባቸው፡፡ ቁጥጥሩ መጥበቅ አለበት፡፡ ፎቆቹ

በአደባባይ ይናገራሉ፡፡ ቤቶቹ በይፋ ያሳብቃሉ፡፡ መሬቶቹ ሊያሸሿቸው የማይችሉ የምዝበራው አካል ናቸው፡፡ ከየት እንደመጣ ማብራሪያ

የማይሰጥበት ሀብት የፊት ለፊት ማስረጃ ነው!! ለባንክ ዕዳ መክፈያ ለሀራጅ የሚቀርቡት ንብረቶች፣ በማያወላውል መልክ በመሞዳሞድ የታጀሉ

ብዝበዛዎችን ያጋልጣሉ!!
‹‹አንድ አንኳር ጨው ውቂያኖስን አያሰማ›› የሚለውን ተረት በጥሞና እያስተዋልን፣ እርምጃው ለጥቂት ጊዜ ብቻ ዘምቶ የሚቆም መሆን

እንደሌለበት መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ ለዚህ ምክንያቱ፤ አንድም ሙስናው ውቂያኖስ አከል በመሆኑ፣ አንድም ሙስና የቀጣይነት ባህሪው

ሥር-ሰደድ በመሆኑ ነው፡፡ ለዚህ የሙስና ሂደት አስተዋፅኦ የሚያደርጉ የመንግሥት አባላት፣ የፓርቲ አባላት፣ ነጋዴዎች፣ ደላሎችና ዐይን

ያወጡ ኤጀንሲዎች ወዘተ … የቢሮክራሲያዊ ካፒታሊዝሙ ፓኮ ውስጥ ያሉ ናቸው። እንዲህ በአገር ደረጃ ኢኮኖሚያዊ ምዝበራን እንዲያጥጥና

እንዲናኝ የሆነው መዝባሪዎቹ ማንን ተማምነው ነው? የሚለውን ጥያቄ ማቅረብ የአባት ነው፡፡ ምነው ቢሉ፤ ‹‹ጌታዋን የተማመነች በግ ላቷን

ውጪ ታሳድራለች›› የሚለው ተረት ፊታችን ድቅን ይላልና! አሁንም ውስጣችንን እንመርምር፡፡ ጥልቅ ተሐድሶ የዕውነት ጥልቅ መሆኑን

በተግባር እናረጋግጥ! ልባዊ እንጂ አፍአዊ አለመሆኑን እናጣራ!
‹‹ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮህንም›› አስብ! ‹‹ባለቤቱን ካልናቁ፣ አጥሩን አይነቀንቁን›› አንርሳ!
“ያሳር እሳት የሚጫረው”
ጥንትም በእፍኝ ጭራሮ ነው!
የሚለውን በመሰረቱ እንገንዘብ፡፡
በሼክስፒር ብዕርና በፀጋዬ ገ/መድህን አንደበት፤
“ነበርን ማለት ግን ከንቱ ነው፣
ተው ነው መጀነኑ በቅቶን፤
ጉራ መንዛት መዘባነን፣
የሚያዛልቅ ዘዴ ባይሆን!”
የሚለውን በጭራሽ አንዘንጋ፡፡
መልካም የጥምቀት በዓል
ክርስትና ዕምነት ተከታዮች!!

በበዓሉ ላይ የምታቀነቅነው የ16 አመቷ ድምጻዊት፣ በአልበም ሽያጭ ቀዳሚ ሆናለች

        ተሸናፊዋን የዲሞክራት ዕጩ ሂላሪ ክሊንተንን ጨምሮ ሶስት የአሜሪካ የቀድሞ ፕሬዚዳንቶች ከሁለት ሳምንት በኋላ በዋሽንግተን ዲሲ በሚከናወነው የዶናልድ ትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ እንደሚገኙ ማረጋገጫ መስጠታቸውን ሲቢኤስ ኒውስ ዘግቧል፡፡
ሂላሪ ክሊንተንና ባለቤታቸው የቀድሞው ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን ባለፈው ማክሰኞ በትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ እንደሚገኙ ያስታወቁ ሲሆን፣ ጂሚ ካርተርና ሌላኛው የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጆርጅ ደብሊው ቡሽም የበዓሉ ታዳሚዎች እንደሚሆኑ ማረጋገጫ መስጠታቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡ በህይወት ከሚገኙት የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች በትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ የማይገኙት ብቸኛ ሰው ትልቁ ቡሽ መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የ92 አመቱ ቡሽ በትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ የማይገኙት በእርጅና እና በጤማ ማጣት ሳቢያ እንደሆነ ማስታወቃቸውንም አስረድቷል። በተያያዘ ዜናም በበዓለ ሲመቱ ላይ የሙዚቃ ስራዎቿን እንድታቀርብ ከአዘጋጅ ኮሚቴው ጥያቄ የቀረበላት ድምጻዊቷ ሬቢካ ፈርጉሰን፣  ግብዣውን ተቀብላ ለመዝፈን ፈቃደኛ የምትሆነው “ስትሬንጅ ፍሩት” የተሰኘውንና በአሜሪካ የሚታየውን ዘረኝነት የሚያወግዘውን የሙዚቃ ስራዋን ለማቅረብ ከተፈቀደላት ብቻ እንደሆነ አስታውቃለች፡፡
የ16 አመቷ አሜሪካዊ ድምጻዊት ጃኪ ኢቫንቾ፤በትራምፕ በዓለ ሲመት ላይ የአሜሪካን ብሄራዊ መዝሙር እንደምታቀርብ መነገሩን ተከትሎም፣ የሙዚቃ አልበም ሽያጭዋ በከፍተኛ ደረጃ ተመንድጎ፣ በአንደኝነት ደረጃ ላይ መቀመጡ ተዘግቧል፡፡ ድምጻዊቷ የትራምፕ በዓለ ሲመት ተሳታፊ መሆኗ በተለያዩ መገናኛ ብዙኃን በስፋት የተዘገበ ሲሆን ይህን ተከትሎም፣ “ድሪም ዊዝ ሚ” እና “ኦ ሆሊ ናይት” የተሰኙት የድምጻዊቷ አልበሞች፣ በቢልቦርድ የደረጃ ሰንጠረዥ በሁለተኛ ደረጃ መቀመጣቸውንም ዘገባዎች ጠቁመዋል፡፡

 ከተማዋ በአመቱ በ21.5 ሚ. ሰዎች ተጎብኝታለች
      የታይላንድ ርዕሰ መዲና ባንኮክ፣ በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2016፣ በርካታ ቁጥር ባላቸው ሰዎች በመጎብኘት ከአለማችን ከተሞች የአንደኛነት ደረጃ መያዟን ፎርብስ መጽሄት ዘግቧል፡፡
በአመቱ ባንኮክን የጎበኙ ሰዎች ቁጥር 21.5 ሚሊዮን እንደደረሰ ማስተርካርድ የተባለው ተቋም ያወጣው አመታዊ ዓለማቀፍ የመዳረሻ ከተሞች ሪፖርት ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፤ በሁለተኛ ደረጃ የተቀመጠቺው ደግሞ በ19.9 ሚሊዮን ሰዎች የተጎበኘቺው ለንደን መሆኗን አስታውቋል። የፈረንሳዩዋ መዲና ፓሪስ በአመቱ በ18 ሚሊዮን ሰዎች በመጎብኘት ከአለማችን ከተሞች የሶስተኛነት ደረጃን የያዘች ሲሆን ዱባይ በ15.27 ሚሊዮን፣ ኒውዮርክ በ12.75 ሚሊዮን፣ ሲንጋፖር በ12.11 ሚሊዮን፣ ኳላላምፑር በ12.02 ሚሊዮን፣ ኢስታምቡል በ11.95 ሚሊዮን፣ ቶክዮ በ11.70 ሚሊዮን፣ ሴኡል በ10.2 ሚሊዮን እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ ይዘዋል፡፡
በአመቱ በ3.6 ሚሊዮን ሰዎች የተጎበኘቺው የደቡብ አፍሪካዋ ጁሃንስበርግ፣ ከአፍሪካ ከተሞች በአመቱ በበርካታ ሰዎች በመጎብኘት ቀዳሚነቱን ስትይዝ፣ ካይሮ በ1.55 ሚሊዮን፣ ኬፕታውን በ1.37 ሚሊዮን ሁለተኛና ሶስተኛ ደረጃ መያዛቸውን ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

ባለፈው ሃምሌ የተቃጣውን የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ተከትሎ ተግባራዊ ያደረገውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከአንድ ወር በፊት (በጥቅምት) ለ3 ወራት ያራዘመው የቱርክ ፓርላማ፤ባለፈው ማክሰኞ ባሳለፈው ውሳኔ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን እንደገና ለ3 ወራት ማራዘሙን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
ፓርላማው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ደጋግሞ ማራዘሙ፣ የአገሪቱ መንግስት ያለ ከልካይ የዜጎችን መብቶች የሚገድቡ ወይም ሙሉ ለሙሉ የሚያሳጡ አዳዲስ ህጎችን ለማውጣትና ተግባራዊ ለማድረግ አስችሎታል ያለው ዘገባው፣ የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ግን፣ አዋጁን ዳግም ማራዘም ያስፈለገው የሽብርተኞች እንቅስቃሴ መቀጠሉን በማጤን ነው ብለዋል፡፡
 ከቀናት በፊት በተከበረው የፈረንጆች አዲስ ዓመት ዕለት የተከሰተው የሽብር ጥቃት 39 ያህል ቱርካውያንን ለሞት መዳረጉን ተከትሎ በአገሪቱ ከፍተኛ ውጥረትና ስጋት የተፈጠረ ሲሆን ፓርላማው በጠራው ስብሰባ፣ አዋጁን እንደገና ለማራዘም መወሰኑን ዘገባው ገልጧል፡፡
የቱርክ መንግስት በሃምሌ ወር ከተቃጣበት መፈንቅለ መንግስት ሙከራ ጋር ንክኪ አላቸው በሚል ከ40 ሺህ በላይ ሰዎችን ማሰሩንና 100 ሺህ ያህል የመንግስት ሰራተኞችን ከስራ ገበታቸው ማባረሩን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአውሮፓ ህብረት የቱርክ መንግስት ያወጣውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በተደጋጋሚ ሲተቸው እንደነበርም አክሎ ገልጧል፡፡

 በወርቅ በተለበጠ የሰርግ ካርድ፣ 50 ሺህ ሰዎች ተጠርተዋል
      በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ህንዳውያን በገንዘብ እጥረት ቀውስ በሚሰቃዩበት በዚህ አስቸጋሪ ወቅት፣ የቀድሞው የህንድ ሚኒስትር ዲኤታ ጋሊ ጃናርዳና ሬዲ፤ 74 ሚሊዮን ዶላር በማውጣት ድል ባለ ድግስ ልጃቸውን መዳራቸው፣በአገሪቱ ዜጎች ዘንድ ከፍተኛ ተቃውሞ እንደገጠመው ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የቀድሞው የቱሪዝም ሚኒስትር ዲኤታ ሴት ልጃቸውን የዳሩበት ይህ ሰርግ፣ በአገረ ህንድ ታሪክ እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ ወጪ ከተደረገባቸው የቅንጦት ሰርጎች አንዱ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ የሰርጉ መጥሪያ ካርድ በወርቅ የተለበጠ፣ ለሰርጉ የተጋበዙ እንግዶች ቁጥርም 50 ሺህ መሆኑን አመልክቷል፡፡
የቅንጦት ሰርጉ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ተቃውሞ መቀስቀሱን ተከትሎ፣ የአካባቢው የግብርና መስሪያ ቤት ባለስልጣናት የግለሰቡን የንግድ ድርጅቶች መዝጋታቸውንና ስለ ሰርጉ ወጪ ማብራሪያ እንዲሰጡ ማድረጉ ተነግሯል፡፡ ሰውዬው ለባለስልጣናቱ በሰጡት ምላሽ፣ በሲንጋፖርና በሌሎች አካባቢዎች ከሚያከናውኑት የቢዝነስ ስራ ባገኙት ገንዘብ፣ የሰርጉን ወጪ መሸፈናቸውንና ለመንግስትም ተገቢውን ግብር በወቅቱ መክፈላቸውን እንደገለጹ ዘገባው አስረድቷል፡፡
ሚኒስትሩ በሙስና ክስ ተመስርቶባቸው ለሶስት አመታት በእስር ላይ ከቆዩ በኋላ፣ ባለፈው አመት በዋስ መፈታታቸውን ያስታወሰው ዘገባው፤ ከእስር ከወጡ በኋላም”ክዛር” የተባለውን የማዕድን አውጭ ኩባንያ ማስተዳደር መቀጠላቸውን ጠቁሞ፣ በርካታ ህንጻዎችና ሌሎች የንግድ ኩባንያዎችመም እንዳሏቸው አስታውቋል፡፡

 የአገር መሪዎች ወደ ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት ምን ይሰሩ እንደነበር ወይም በምን ሙያ ላይ ተሰማርተው እንደቆዩ አስባችሁት ታውቃላችሁ? እኔ ትዝ ብሎኝም አያውቅም፡፡ ግን እኒህ ሰዎች ሲወለዱ ፕሬዚዳንት ወይም ጠ/ሚኒስትር ሆነው አለመወለዳቸውን ያለ ጥርጥር እናውቃለን፡፡ (የንጉሳውያን ቤተሰብ ካልሆኑ በቀር) ይሄ ማለት ደግሞ ወደ ሥልጣን እስኪመጡ ድረስ ባለው ዕድሜያቸው ሲተዳደሩ የቆዩበት ሙያ እንደሚኖራቸው ይጠቁማል፡፡ አንዳንዴ ታዲያ ተሰማርተው የነበሩበት ሙያ ወይም የሥራ ዘርፍ ከፖለቲካና ከአገር መሪነት ጋር ባለው ከፍተኛ ርቀት የተነሳ መገረምና መደነቅ ሊፈጥርብን ይችላል፡፡ የሚከተሉት መሪዎች ማለፊያ ምሳሌዎች ይመስሉኛል፡፡
                                  
     ሙዚቃ ቀማሪው ፕሬዚዳንት
 -   የክሮኤሽያው ፕሬዚዳንት ኢቮ ጆሲፖቪክ፤ወደ ፖለቲካ  ከመግባታቸው በፊት የክላሲካል ሙዚቃ ቀማሪ ነበሩ፡፡ በደርዘን የሚቆጠሩ ክላሲካል ሙዚቃዎችን የደረሱ ሲሆን የክሮኤሽያን ዋነኛ የሙዚቃ ፌስቲቫል መርተዋል፡፡  
•   ጆሲፖቪክ በፕሬዚዳንትነት የተመረጡት እ.ኤ.አ በ2010 ሲሆን በወቅቱ የሙዚቃ ሙያቸውን እንደማያቆሙ ቃል ገብተው ነበር። በኋላ ላይ ግን የፕሬዚዳንትነት ስራቸው ፋታ የማይሰጥ በመሆኑ ቃላቸውን መፈፀም እንዳልቻሉ አምነዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን አንድ ፒያኖ  ወደ ፕሬዚዳንታዊ ቢሮአቸው ለማስገባት አልሰነፉም፡፡ ኢቮ ጆሲፖቪክ፤ በቅድመ ምርጫ ቅስቀሳ ወቅት ኪ-ቦርድ መጫወታቸው ተዘግቧል፡፡
    ሰዓሊው ጠ/ሚኒስትር
 -   የአልባኒያው ጠ/ሚኒስትር ኢዲ ራማ ወደ አገር መሪነት ሥልጣን ከመምጣታቸው በፊት ሰዓሊ ነበሩ፡፡ በፓሪስ የሥነ  ጥበብ ት/ቤት ስዕል ያጠኑት ራማ፤ እ.ኤ.አ በ1998 ወደ አልባኒያ ሲመለሱ የባህል ሚኒስትር ሆነው ተመደቡ። ከዚያም የአልባኒያ ከተማ- ቲራና፣ ከንቲባ ሆነው ተሾሙ፡፡ ይሄም ለሥነ ጥበባዊ ውበት ያላቸውን ስሜት ለመወጣት ዕድል የሰጣቸው ሲሆን በሲሚንቶ የተገነቡ የኮሙኒስት ዘመን ግራጫ ህንፃዎች፤ በሮዝ፣ በብጫ፣ በአረንጓዴና ሀምራዊ ቀለማት እንዲዋቡ አስደርገዋል፡፡
•   የቀድሞ የቅርጫት ኳስ ተጫዋችም የነበሩት ራማ፤ እ.ኤ.አ በ2004 ለቢቢሲ በሰጡት  ቃለ መጠይቅ፤ “በእርግጠኝነት ፖለቲከኛ ነኝ ለማለት አልችልም፡፡ እኔ አሁንም ሰዓሊ ነኝ ነው የምለው፤ ፖለቲካን ለለውጥ በመሳሪያነት ለመጠቀም እየሞከርኩ ነው” ብለው ነበር፡፡
•   በ2012 የTED ቶክ ላይ ለመሪዎች ባስተላለፉት ጥሪ፡- “ከተማችሁን በቀለም መልሳችሁ ፍጠሩ” ብለዋል፡፡  
   ገጣሚው ፕሬዚዳንት
 -   የአየርላንድ ፕሬዚዳንት ማይክል ዲ.ሂጌንስ፣ የሥልጣን መንበር ከመቆናጠጣቸው በፊት ገጣሚ ነበሩ፡፡ አራት የግጥም ጥራዞችን (volumes) ለህትመት ያበቁ ሲሆን የአየርላንድ የመጀመሪያው የሥነ ጥበብ ሚኒስትርም ነበሩ። ማይክል ዲ. በሚል ቁልምጫ የሚታወቁት ታጋይ-ገጣሚ ፕሬዚዳንቱ፤ አየርላንድ “የፈጠራ ሪፑብሊክ” እንድትሆን ጠይቀዋል፡፡  
•    የራሳቸው የግጥም ስራዎች ግን ከሃያስያን የሰላ ትችት አላመለጡም፡፡ አንዱ ሃያሲ እንደውም፤ “ፕሬዚዳንቱ በሥነ ፅሁፍ ላይ ለፈፀሙት ወንጀል ክስ ሊመሰረትባቸው ይችላል” ማለቱ ተዘግቧል፡፡

Friday, 06 January 2017 12:32

የቢዝነስ ጥግ

- ባለፀጋ ለመሆን ከፈለግህ፣ ተኝተህም ገንዘብ መስራት አለብህ፡፡
      ዴቪድ ቤይሊ
- አበዳሪም ተበዳሪም አትሁን፡፡
     ዊሊያም ሼክስፒር
- ገንዘብ ማስቀመጥ ስህተት ከሆነ፣ ትክክል መሆን አልፈልግም፡፡
    ዊሊያም ሻትነር
- ከባለፀጎች የምወድላቸው ገንዘባቸውን ብቻ ነው፡፡
    ናንሲ አስቶር
- ሀብታም ብዙ አዱኛ ያለው ሳይሆን ብዙ የሚሰጥ ሰው ነው፡፡
    ኤሪክ ፍሮም
- ሀብታም የሚያደርግህ ደሞዝህ ሳይሆን የአወጣጥ ልማድህ ነው፡፡
   ቻርልስ ኤ. ጃፌ
- ህይወት በዶላር ኖት ላይ መታተም የለበትም፡፡
   ክሊፎድ ኦዴትስ
- የምንኖረው በወርቃማው ህግ ነው፡፡ ወርቁ ያላቸው ህጉን ያወጡታል፡፡
   ቡዚ ባቫሲ
- ሴቶች ባይኖሩ ኖሮ በዓለም ላይ ያለው ገንዘብ በሙሉ ትርጉም አይኖረውም ነበር፡፡
   አሪስቶትል ኦናሲስ

የፈረንሳዩ  ሎቨር ግሩፕ፤  ከ480 ሚ.ብር በላይ በሆነ ወጪ በአዲስ አበባ በመገንባት ላይ ያለውን  “ሮያል ቱሊፕ ፕላዛ” ባለ 5 ኮከብ ሆቴል ለማስተዳደር፣ ”በገዝ ቢዝነስ ግሩፕ” ከተሰኘ የኢትዮጵያ ኩባንያ ጋር ተስማማ፡፡ ግንባታው በመጠናቀቅ ላይ የሚገኘው ሆቴሉ፤ 88 የመኝታ ክፍሎች እንዳሉት ታውቋል። ሆቴሉ የሬስቶራንት፣ የስፓ፣ የስብሰባ አዳራሽ (ለቢዝነስና ተጓዦች) አገልግሎቶችን ጨምሮ ሌሎች ደረጃቸውን የጠበቁ፣ የላቁ መስተንግዶዎችንም ያቀርባል ተብሏል፡፡
ሎቨር ሆቴልስ ግሩፕ፤ ሁለተኛውን ባለ 5 ኮከብ “ሮያል ቱሊፕ ፕላዛ” ሆቴል በኢትዮጵያ መክፈቱ፤ ሎቨር በአፍሪካ ያቀደውን ሆቴሎቹን የማስፋፋት ስትራቴጂ ያጠናክርለታል ተብሏል፡፡ በኬንያ፣ ሩዋንዳ እንዲሁም በታንዛንያ የሆቴሎቹን ቁጥር እያሳደገና አገልግሎቱን እያስፋፋ ይገኛል፡፡ በ2017 እ.ኤ.አ ሎቨርስ ሆቴልስ፤ ወደ 15 ተጨማሪ ሆቴሎችን በክልሉ ለመክፈት አቅዷል፡፡  
ሉቨር ሆቴል ግሩፕ ከሚያስተዳድራቸው ሶስት የሆቴል ብራንዶች አንዱ የሆነውን “ጎልደን ቱሊፕ” ከጥቂት ዓመታት በፊት በቦሌ ከፍቶ እያስተዳደረ ሲሆን “ሮያል ቱሊፕ” የተሰኘው ብራንድ በአዲስ አበባ እንዲከፈት ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀ ድርድር መካሄዱ በስምምነት ፊርማው ላይ ተገልጿል፡፡ ሆቴሉ በአዲስ አበባ እንዲከፈት ድርድሩን ያካሄደው በቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ ቢዝነስ ላይ የተሰማራው “አዚ ቢዝነስና ሆስፒታሊቲ ማኔጅመንት ግሩፕ” መሆኑን የ”ኦዚ ቢዝነስ ሆስፒታሊቲ ግሩፕ ማኔጅምነት” ዋና ዳይሬክተር አቶ ቁምነገር ተከተል ገልጸዋል፡፡
የሆቴሉ በአዲስ አበባ መከፈት ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣውን የአገሪቱን የጎብኚ ፍሰት ለማስተናገድና አለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ መስተንግዶ ለመስጠት ትልቅ ሚና ይኖረዋል ተብሏል፡፡ ሆቴሉ ተጠናቅቆ አገልግሎት መስጠት ሲጀምር ለበርካታ ኢትዮጵያውያን ከፍተኛ የስራ እድል እንደሚፈጥርም ተጠቁሟል፡፡

  የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዛሬ የሚከበረውን የገና በዓል ምክንያት በማድረግ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ቅጥር ግቢ ውስጥ ለሚገነባው የልብ ህሙማን ማዕከል የ2.6 ሚ. ብር ድጋፍ ማድረጉን ገለፀ፡፡ ባንኩ በገና ዕለት የሚተላለፍ የበዓል የቴሌቪዥንና የሬዲዮ ፕሮግራም ያዘጋጀ ሲሆን የበዓሉ ቅድመ ቀረፃም ባለፈው ማክሰኞ ረፋድ ላይ በልብ ህሙማን ማዕከል አዳራሽ መከናወኑን የቀረፃውም ምክንያት የገንዘቡ ልገሳ እንደሆነ ባንኩ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ባንኩ በልብ ህመም የሚሰቃዩ ጨቅላ ህፃናትን ለመታደግ ከማዕከሉ ጋር አብሮ እየሰራ መሆኑን ከዚህ ቀደም ድጋፍ ማድረጉን ያስታወሱት የባንኩ ተቀዳሚ ስራ አስኪያጅና ኮሚዩኒኬሽን ሃላፊ አቶ በልሁ ታከለ ይህኛው ድጋፍ የገና በዓልን ምክንያት በማድረግ የተደረገ የልገሳ ልዩ ስነ ስርዓት እንደሆነም ጨምረው ገልፀዋል፡፡
ባንኩ በቀጣይም ለማዕከሉ ድጋፍ ማድረጉን እንደሚቀጥል ለማወቅ ተችሏል፡፡