
Administrator
ቀረች ቢሉኝ
ለካ ከልቤ እወድሽ ነበር
ለካስ ከልቤ አፈቅርሻለሁ
ከእውነት እንደማስብሽ
ከአንጀቴ እንደናፈቅኩሽ
ዛሬን ለኔ አውቄዋለሁ፡፡
ዛሬን ነገን ትመጪ እያልኩ
ቀን ስቆጥር እየኖርኩኝ…
አንቺን ከማሰቤ ጋር
አንቺን ከናፍቆቴ ጋር
እያሰብኩሽ እያለምኩ
መልክሽን ይዤ እየዋልኩ
ሰውነትሽን ይዤ እያቀፍኩ
ሳወራልሽ እያደርኩኝ…
ዛሬ ነገ ላገኝሽ
ቀኔን ስቆጥር እየኖርኩኝ
ቀረች ቢሉኝ
መቼ ደርሰሽ
መች አግኝቼሽ
የልቤን ቃል
ላጫውትሽ፡፡
እስክትመጪ አጠራቅሜ
አስቀምጬ ያቆየሁሽን
የፍቅራችንን ምስጢር
ተቃቅፈን “ምናወራትን
ምንንሾካሾካትን
መቼ ደርሰሽ እያልኩ እኔ
ቀኑ ረዝሞ ሌ ቱ ጨንቆኝ
ላንቺ ብዬ ተካፍዬ
ለሌላ የማልነግረውን
ጭንቀቴን ሃሳቤን ሁሉ
ሳሰላስል የኖርኩትን
ሳላዋይሽ ቀረች ቢሉኝ
ምን ሊውጠኝ?
ታህሳስ 18/1980
(“ሶረኔ” ልዩ ልዩ የበረሃ ግጥሞች
ከሚለው መድበል የተወሰደ)
“The Ethics of Zara Yacob” ረቡዕ ይቀርባል
በር አባ ዳዊት ወርቁ የተፃፈው “The Ethics of Zara Yacob” እንዲሁም በአባ ብሩክ ወልደገብር እና አባ ማርዮ አሌክሲስ ፓርቴላ የተዘጋጀው “Abyssinian Christianity. The First Christian Nation?” መጽሐፍ በመጪው ረቡዕ እንደሚመረቁ የቅዱስ ቶማስ አኩዊናስ የኢትዮጵያ ካቶሊክ ዩኒቨርሲቲ አስታወቀ፡፡ የሁለቱ መጻሕፍት ማስተዋወቂያ ዝግጅት የሚካሄደው አስኮ በሚገኘው የቅዱስ ፍራንሲስ ካቶሊክ ገዳም ካፑቺን ፍራንሲስ የጥናትና ሥልጠና ማእከል አዳራሽ ነው እንደሚከናወን ታውቋል፡፡
“ጋይድ መጋዚን” በነፃ እየተሰራጨ ነው
ኢትዮጵያን ለሚጐበኙ የውጭ ሀገር ጐብኚዎች የሚያገለግል የመምሪያ መጽሐፍ አሳትሞ ማሰራጨት መጀመሩን “ኬር ኤዢ ኢትዮጵያ” አስታወቀ፡፡ በእንግሊዝኛ እና በእስፓኒሽ ቋንቋ የታተመው የጐብኚዎች መምሪያ መጽሐፍ ግማሽ ሚሊዬን ብር ወጥቶበታል ያሉት አዘጋጆቹ፤ መጽሐፉ ኢንዱስትሪውን ቢያነቃቃም በውጭ ሀገር ታትሞ ወደሀገር ሲገባ የመንግስት ተቋማት አላበረታቱንም ብለዋል፡፡ አብዛኞቹን ማስታወቂያዎችም በነፃ ያሳተሙ መሆናቸውን ለዝግጅት ክፍላችን ተናግረዋል፡፡
በwww.ker_ezhiethiopia.com የሚገኘው መጽሔት 20ሺህ ቅጂ የታተመ ሲሆን ቅጂው ከራስ ሆቴል እና ሌሎች ትልልቅ ሆቴሎች በነፃ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡
ላፍቶ ጋለሪ የ40 ሴት ሰዓሊያን ሥራዎችን እያሳየ ነው
ላፍቶ ጋለሪ ከአርባ በላይ የሴት ሰዓሊያን ሥራዎችን ያካተተ “Inspired women2” የተሰኘ የስዕል አውደርዕይ ከትላንት በስቲያ ለተመልካች ማቅረብ ጀመረ፡፡ ኢትዮጵያውያንና የውጭ አገር ሴት ሰዓሊያን የተሳተፉበት አውደርዕይ ከ150 በላይ የስዕል ስራዎች የያዘ ሲሆን ለአንድ ወር ለህዝብ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡
የኃይለመለኮት መዋዕል “እንካስላንቲያ” ለንባብ ቀረበ
በአንጋፋው ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል የተዘጋጀ “እንካስላንቲያ” የተሰኘ መፅሃፍ ሰሞኑን ለንባብ ቀረበ፡፡ ደራሲው ስለ መፅሃፉ ፋይዳ በገለፀበት መግቢያ፤ “የእንካስላንቲያ ሥነ-ቃል የግጥማዊ ዜማነት ባህሪይ ስላለው ወጣቶች እየተፈራረቁና እየተፎካከሩ በመሳተፍ አያሌ ቁምነገሮችን … ይማሩበታል” ብሏል፡፡
በ107 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፤ ዕውቀት፣ ዲሞክራሲ፣ ሙስና፣ ፍትህ ወዘተ በሚሉ ርዕሶች ስር የተዘጋጁ እንካስላንቲያዎችን የያዘ ሲሆን በ20 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ ኃይለመለኮት መዋዕል “ጉንጉን” እና “የወዲያነሸ” በተባሉት ተወዳጅ የረዥም ልብወለድ ሥራዎቹ ይታወቃል፡፡
“ግጥም በጃዝ” ረቡዕ ይቀጥላል
ባለፈው ሚያዝያ 2 መቅረብ የነበረበትና ታዳሚዎች በሥፍራው ከተገኙ በኋላ የተቋረጠው “ግጥም በጃዝ” በመጪው ረቡዕ እንደሚቀጥል አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ ቅድመ ዝግጅት አጠናቀን ልናቀርብ ከተዘጋጀን በኋላ የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ተቆጣጣሪ አካል ፈቃድ የላቸውም በማለቱ ስለሌላቸው አያቀርቡም በሚል ለራስ ሆቴል ዝግጅቱ መቋረጡን ተናግረዋል፡፡ ረቡዕ ከቀኑ 11 ሰዓት በሚቀጥለው “21ኛው ግጥምን በጃዝ” ዝግጅት ላይ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፣ ሞገስ ሀብቱ፣ ምስራቅ ተረፈ፣ በረከት በላይነህ፣ ግሩም ዘነበ በግጥም፤ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት በወግ ይሳተፋሉ፡፡
የሕይወት ስንቅ
ከ1/3ኛ በላይ የህፃናት ሞትን በክትባት መከላከል ይቻላል
የፈንጣጣ በሽታ በኢትዮጵያ መኖሩ በታወቀ ጊዜ ከፓሪስ የህክምና ፋኩሊቲ የተውጣጡ ቡድኖች ህዝቡን ለመከተብ በሚል በ1890 ዓ.ም አዲስ አበባ ገቡ፡፡ ያኔ ህብረተሰቡ ስለ ፈንጣጣ በሽታም ሆነ ስለሚሰጠው ክትባት ምንም ግንዛቤ ስላልነበረው፣ ክትባቱን ለመውሰድ ፈቃደኛ አልነበረም፡፡ ይህንን ሁኔታ ለመቀየርና ህዝቡን ለመቀስቀስ አጤ ሚኒልክ የፈንጣጣውን ክትባት በፈረንሳዮች እጅ ተከተቡ። ይህ ሁኔታ ግን የክትባትን ጠቀሜታ ህብረተሰቡ በአግባቡ እንዲረዳና ክትባቱን ለመውሰድ ፈቃደኛ እንዲሆን ባለማድረጉ ንጉሱ አዋጅ አስነገሩ፡፡ “አሁን በከተማው ፈንጣጣ ገብታ ሰውን ሁሉ እንደምትፈጅ ታያላችሁ፡፡
ይህቺንም ክፉ በሽታ ከአገር ለማጥፋት በከተማ ያለው ሰው አዋቂውም ልጁም ከከብት ሃኪም ዘንድ ወይም ከሆስፒታል እየሄደ ይከተብ፡፡ ለመከተብ ዋጋ አያስከፍልም። ጊዜም አያስፈታ፡፡ ከአምስት ደቂቃም ይበልጥ አያቆይ፡፡ አሁንም ለራሳችሁና ለልጆቻችሁ የምታስቡ ሰዎች ሁሉ ተከተቡ፡፡ ሳትከተቡ ቀርታችሁ ሰው ቢሞትባችሁ በስንፍናችሁ መሆኑን እወቁት” ይህ የአጤ ሚኒሊክ አዋጅ መጋቢት 2ቀን 1904 ዓ.ም በገበያ መሃል እንዲነበብ ተደረገ፡፡ በማግስቱ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሰዎች ውርዝ እየተባለ በሚጠራውና በወቅቱ ክትባቱን ይሰጥ በነበረው ሐኪም መኖሪያ ቤትና የሥራ ቦታ ይሰባሰቡ ጀመር፡፡ ስለሁኔታው ውርዝ የተባለው ይኸው ፈረንሳዊ ሐኪም ሲናገር፤ “አዋጁ በተነበበ ማግስት ከተለያዩ አቅጣጫዎች በርካታ ሰዎች ወደ ቤቴ ይመጡ ጀመር፡፡ የአምስትና የስድስት ቀናት ጉዞ አድርገው አዲስ አበባ የሚመጡት ሰዎች ተራ ደርሷቸው እስኪከተቡ ድረስ በቤቴ አካባቢ በመስፈራቸው በራፌ ላይ ዘብ አቆምኩ፡፡ ከየካቲት ወር እስከ ነሐሴ ድረስም 20ሺ 700 ሰዎችን አዲስ አበባ ውስጥ ከተብን” ማለቱን ጳውሎስ ኞኞ “አጤ ሚኒልክ” በተሰኘው መፅሃፉ ላይ አስፍሮታል፡፡ በኢትዮጵያ ዘመናዊ የክትባት ታሪክም በአፄ ሚኒልክ ዘመነ መንግሥት የተሰጠው ክትባት የመጀመሪያ ነው፡፡
ክትባቶች በተለያዩ አይነቶች ተዘጋጅተው ወደሰውነታችን እንዲገቡ ከተደረጉ በኋላ የሰውነታችንን በሽታ የመከላከል አቋም (“Immunity”) የሚያሳድጉ የህክምና ጥበቦች ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ በ1769 ዓ.ም ኤድዋርድ ጅነር በተባለ ሰው አማካይነት ለመጀመሪያ ጊዜ በጥቅም ላይ የዋለው ክትባት የተሰራው ከከብት ቫይረስ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይህ ከከብት ቫይረስ ተሰርቶ ጥቅም ላይ መዋል የጀመረው ክትባት፤ በየጊዜው የተለያዩ ለውጦችንና መሻሻሎችን እያሳየ በመሄድ ዛሬ ከደረሰበት ደረጃ ላይ ሊደርስ ችሏል፡፡ ክትባቶች አይነታቸውም ሆነ መጠናቸው የተለያየ ሲሆን የአሰጣጥ ሂደታቸውም ክትባቱን የሚወስደውን ሰው እድሜ መሰረት ያደረገ ነው፡፡ የአለም ሀገራት ህዝባቸውን መሰረት ባደረገ መልኩ ለክትባት አመራረትም ሆነ አሰጣጥ ፖሊሲዎችን ያረቃሉ፡፡ በተለያዩ ህጐች፣ መመሪያዎችና ደንቦች መሰረትም ሊመሩ ይችላሉ፡፡ በዓለም አቀፍ ስምምነቶች መሰረት ግን እነዚህ ፖሊሲዎችና መመሪያዎች የትኛውንም ህዝብ የክትባቱ ተጠቃሚ እንደሚያደርጉ ማረጋገጥ ይጠበቅባቸዋል፡፡
ለኩፍኝ፣ ለፖሊዮ፣ ለመንጋጋ ቆልፍና ዘጊ አናዳ የመሳሰሉትን በሽታዎች ለመከላከል የሚሰጡት ክትባቶች፣ የአለም ህዝቦችን አስከፊ ወደሆነ የወረርሽኝ ጥቃት እንዳይገቡ ትልቅ ጠቀሜታ ይኖራቸዋል ተብሎ ይታመናል፡፡ ኢትዮጵያ የክትባት አገልግሎትን ለህዝቦቻቸው ለማዳረስ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ ከሚገኙ የአለም አገራት መካከል አንዷ ናት፡፡ በአገሪቱ ከሚከሰቱት የህፃናት ህመምና ሞት መካከል አንድ ሶስተኛው የሚሆኑት በክትባት መከላከል በሚቻል በሽታዎች አማካይነት የሚፈጠሩ ናቸው፡፡ ህብረተሰቡ በክትባት ላይ ያለው ግንዛቤ አነስተኛ በመሆኑና አገልግሎቱም በአስተማማኝና በበቂ መጠን ባለመዳረሱ ምክንያት ዛሬም ድረስ በርካታ ህፃናት በክትባት ሊወገዱ በሚችሉ በሽታዎች እየተጠቁ ለህመም፣ ለአካል ጉዳትና ለሞት ሲጋለጡ ይስተዋላል፡፡ “ህፃናትን በማስከተብ ከህመም፣ ከአካል ጉዳትና ከሞት እንጠብቃቸው” በሚል መሪ ቃል ከሚያዝያ 14-20 ቀን 2005 ዓ.ም በአገራችን ለሦስተኛ ጊዜ የሚከበረውን የአፍሪካ የክትባት ሳምንት አስመልክቶ የፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ሰሞኑን በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ አገሪቱ ክትባትን ለህብረተሰቡ ሁሉ በበቂ መጠን ለማዳረስ ጥረት እያደረገች ነው፡፡
የክትባት ሽፋኑና አገልግሎቱ በአስተማማኝነት ያደገና የጉዳት መጠኑ የቀነሰ ቢሆንም በየደረጃው ያለው የህብረተሰቡ ግንዛቤ ባለማደጉ ምክንያት በክትባት ሊወገዱ የሚችሉ በሽታዎች በርካታ ህፃናትን ለአካል ጉዳትና ለሞት እያጋለጡ ይገኛሉ፡፡ ሚኒስትር መ/ቤቱ እንደ ኩፍኝ የመሳሰሉ ወረርሽኞችን ለማስቆም፣ በሁሉም የጤና ድርጅቶች ያለምንም ክፍያ ክትባትን ለህፃናት በማዳረስ ላይ መሆኑንም በዚሁ ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ አስታውቋል። በአገሪቱ የሚገኙት ከ250 በላይ ሆስፒታሎች፣ 3ሺህ ጤና ጣቢያዎችና 25ሺ ጤና ኬላዎች ክትባትን ለህብረተሰቡ በማዳረሱ ረገድ ቁልፍ ሚና እንዳላቸውም በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር የህዝብ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተሩ አቶ አህመድ ኢማም ተናግረዋል፡፡ የአገሪቱ የመደበኛ ክትባት ፕሮግራም ሽፋን እ.ኤ.አ በ2003 ከነበረበት 52 በመቶ እድገት አሳይቶ 86 በመቶ መድረሱንም ጋዜጣዊ መግለጫው ይፋ አድርጓል፡፡ የበሽታዎችን ስርጭት በቀላሉ ለመቆጣጠርና ጤናማ ትውልድ ለማፍራት ትልቅ ጠቀሜታ አለው የሚባለውን የክትባት አገልግሎት ስርጭትና ጥራት በተመለከተ ለግንዛቤ የሚረዱ አንዳንድ መረጃዎችን በሥራ አጋጣሚ በተዘዋወርንባቸው አካባቢዎች ለማሰባሰብ ሞክረን ነበር፡፡ በሐረርጌ ዞን አፈር ደባ ሶፊ ወረዳ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ያገኘኋት የአምስት ልጆች እናት፣ የ39 አመቷ ዘሀራ የሱፍ የወለደቻቸው አምስቱም ልጆቿ ክትባት አለመከተባቸውንና ልጆቿን ለማስከተብ የሚያስችል ገንዘብ እንደሌላት ነግራኛለች።
ክትባቱ በሁሉም የጤና ጣቢያዎችና የጤና ኬላዎች ያለክፍያ እንደሚሰጥ የሰማሁትን ብነግራትም በጄ አላለችኝም፡፡ “የእከሌ ልጅ አልተከተበችም፣ እከሌም ልጇን አላስከተበችም፡፡ ግን ምንም አልሆኑባትም፡፡ ለምን አስከትባለሁ” መልሳ ጠየቀችኝ፡፡ ክትባት ለወደፊቱ የልጆቿ ጤናማ ህይወት መሰረት መሆኑንና በወረርሽኝ መልክ ከሚከሰቱ በሽታዎች በቀላሉ መዳን እንደሚቻል ብነግራትም ሃሳቤ ሊዋጥላት አልቻለም፡፡ ይሄ የሚያሳየው በጤናው ዘርፍ የሚሰሩ መንግሥታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የህብረተሰቡን ግንዛቤ ለማሳደግ በበቂ ሁኔታ አለመንቀሳቀሳቸውን ይመስለኛል፡፡ በምዕተ አመቱ የልማት ግብ ተደርገው ከተያዙት ጉዳዮች መካከል አንዱ የሆነውና እድሜያቸው ከአምስት አመት በታች የሆኑ ህፃናትን ሞት መቀነስ የሚለውን ጉዳይ ለማሳካት ሁሉም በዘርፉ የሚንቀሳቀሱ ባለድርሻ አካላት ብዙ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ክትባቶች በበቂ ሁኔታ መሰራጨታቸውን ብቻ ሳይሆን፣ ህብረተሰቡ ስለ ክትባት ጠቀሜታ በአግባቡ ተረድቶ በጊዜውና በወቅቱ ልጆቹን እንዲያስከትብ ለማድረግ በመጀመርያ ግንዛቤውን ማሳደግ ዋንኛ ተግባር ነው። ከዚህ በተጨማሪም ለህብረተሰቡ እንዲደረሱ በየአካባቢው የሚሰራጩት ክትባቶች ጥራትና ወደ ተጠቃሚው የሚደርሱበት ሁኔታ ምን ያህል አስተማማኝ ነው የሚለውን ማየትም ግድ ይላል፡፡
በጥንቃቄ ጉድለት የተበላሹ ክትባቶች ከጥቅማቸው ጉዳታቸው ያመዝናልና ትኩረት ሊሰጠው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ ክትባቶች ከተመረቱበት ቦታ ጀምሮ ወደ ተጠቃሚው እስከሚደርሱበት ጊዜ ድረስ ያለው ሂደት ቀዝቃዛው ሰንሰለት (Cold chain) በሚል መጠሪያ ይታወቃል፡፡ ክትባቱ ተመርቶ ውጤታማ የሆነ አገልግሎት እንዲሰጥ ለማድረግም፣ ይህ ሰንሰለት ሂደቱን ጠብቆ በአግባቡ ተግባራዊ መደረግ ይኖርበታል፡፡ ቀዝቃዛውን ሰንሰለት መሰረት ባደረገ መልኩ ጥቅም ላይ ያልዋለ ክትባት መድሃኒትነቱ አስተማማኝ አይሆንም፡፡ የማቀዝቀዣ እጦት በድሃ አገራት ክትባትን በበቂ መጠን ለማዳረስ ትልቅ እንቅፋት ሲሆን የሚስተዋለውም ለዚህ ነው፡፡ ይህንን ችግር ለማስወገድና ያለፍሪጅ በመቆየትና ከቦታ ቦታ በመዘዋወር አገልግሎት ላይ ለመዋል የሚችሉ ክትባቶችን ለማምረት ሳይንቲስቶች ከመትጋት አልቦዘኑም፡፡ ሔፒታይተስ ቢ የተባለውን ገዳይ በሽታ ለመከላከል ያስችላል የተባለውን ክትባትም በድንች ዘሮች ውስጥ በማስገባትና በማምረት ለምግብነት ማዋል ጀምረዋል፡፡ እነዚህን ድንቾች በተመገቡ ሰዎች ላይ በተደረገ ጥናት መሰረትም 60 በመቶ የሚሆኑት የድንቹ ተመጋቢዎች ሔፒታይተስ ቢ የተባለውን በሽታ ለመከላከል የሚያስችላቸው (Anti Bodies) በደማቸው ውስጥ ተገኝቷል፡፡
ይሁን እንጂ ሳይንቲስቶቹ እነዚህን ክትባት የያዙ ድንቾችን በስፋት ለማምረትና ለማሰራጨት እንቅፋት ይሆናሉ የሚሏቸው ችግሮችም አሉ፡፡ ከእነዚህ መካከልም የአወሳሰድ መጠኑ (Dosage) አለመመጠን አንዱ ሲሆን ሌላው ደግሞ ድንቾቹ ከሌሎች ለምግብነት ከሚውሉ ድንቾች ጋር ተቀላቅለው ለተራ ምግብነት ሊውሉ ይችላሉ የሚለው ስጋት ነው፡፡ ያም ሆነ ይህ በሚበሉ ምግቦች መልክ እየተዘጋጁ ጥቅም ላይ እንዲውሉ የሚደረጉት የክትባት አይነቶች እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ድሃ አገራት ውስጥ ክትባትን ለማዳረስ እንቅፋት የሆነውን የፍሪጅ አገልግሎት ለማስቀረት ትልቅ ጠቀሜታ ይኖራቸዋል፡፡ የፌደራል ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ አሁን በአገሪቱ እየተሰጡ ያሉትን ዘጠኝ አይነት ክትባቶች በቁጥር ከፍ ለማድረግ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኝም አስታውቋል፡፡ አሁን በአገሪቱ በስፋት እየተሰጡ ከሚገኙ የክትባት አይነቶች መካከል ፖሊዮ፣ ኩፍኝ፣ መንጋጋ ቆልፍ፣ ዘጊ አናዳ፣ ማኔንጃይትስና ሔፒታይተስ ቢ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡
“ዝናብ የለም፤ ደመና ነው፤ ሙቀት የለም…”
(ስለምርጫው የተሰጠ አስተያየት)
እንካ ስላንቲያ?
በምንቲያ?
በረገጣ! ምናለ በረገጣ?
በህዝባዊ አመራር መድበል ካላመጣ እያደር ይፋጃል ያንድ ፓርቲ ጣጣ!! ሰሞኑን እጄ የገባው መፅሃፍ ለየት ያለ ነው፡፡ ከአሁን ቀደም እንዲህ ያለ መፅሃፍ መውጣቱን አላውቅም፡፡ “እንካስላንቲያ” ይላል የመፅሃፉ ርዕስ፡፡ ደራሲው ግን ዝነኛ ነው፡፡ “ጉንጉን” እና “የወዲያነሽ” በተባሉት ወርቅ የልብወለድ ሥራዎቹ ይታወቃል፡፡ አንጋፋው ደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል! እኔማ እንዴት አሰበው አስብሎኛል፡፡ ቁጭ ብሎ እንካ ስላንቲያ መፍጠር እኮ ቀልድ አይደለም፡፡ ትዕግስት ይጠይቃል፡፡ በዚያ ላይ የመረጣቸው ርዕሰ ጉዳዮች ከበድ የሚሉ ናቸው፡፡ እስኪ አስቡት --- ዕውቀት፣ዲሞክራሲ፣ ህዝብ፣ ፍትህ፣ የህግ የበላይነት፣ ሙስና ወዘተ … ርዕሶች ላይ ያተኮሩ እንካስላንቲያዎቿን ነው ያዘጋጀው፡፡ መፅሃፉን እየኮመኮምኩ ሳለ አንድ ሃሳብ ብልጭ አለልኝ፡፡ ሃሳቡ ለማን መሰላችሁ የሚጠቅመው? ለኢቴቪ ነው! እናላችሁ --- ኢቴቪ ለምን “የእንካስላንቲያ ውድድር” አያካሂድም ብዬ አሰብኩ፡፡ ፕሮፓጋንዳውንም ቢሆን እኮ በእንካስላንቲያ አጣፍጦ ቢያቀርብልን ይሻለናል!! በዛውም ትንሽ ብንዝናና ምናለበት፡፡ በነገራችሁ ላይ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ቢሆኑ የምርጫ ክርክር ሲያካሂዱ በእንካስላንቲያ ቢያደርጉልን ሳይሻለን አይቀርም (ምርጫው የታለና እንዳትሉኝ ብቻ!) በተለይ እንዳሁኑ ኢህአዴግ ያመዘነበት ምርጫ ሲሆን እንካስላንቲያው ሞቅ ደመቅ የሚያደርገው ይመስለኛል፡፡ (ፓርላማውንም ምርጫውንም ተቆጣጠረው አይደል?) ከሁሉም በላይ ደግሞ ከ97 ምርጫ ወዲህ ጥቅልል ብሎ የተኛውን ፖለቲካችንን ከእንቅልፉ ለመቀስቀስም ማለፊያ ዘዴ ይመስለኛል - ፖለቲካን በእንካስላንቲያ ማስኬድ! ወጋችንም እንደ ዘንድሮ ምርጫና ፖለቲካ ጭር እንዳይል … ለምን በጥቂት እንካስላንቲያዎች ሞቅ ደመቅ አናደርገውም - እድሜ ለደራሲ ኃይለመለኮት!
እንካስላንቲያ?
በምንቲያ?
በወለምዘለም!
ምን አለህ በወለምዘለም?
አንጠርጥረህ ምረጥ በምርጫ ቀልድ የለም፡፡ አያችሁልኝ … ምርጥ የምርጫ ማስታወቂያ! ትንሽ ዘገየ እንጂ የአዲስ አበባ መስተዳድር ይጠቀምበት ነበር፡፡ በቅርቡ ሲያቀርበው የነበረው ግን ግግም ያለ ነው - እንድ ድራማቸው! ባይገርማችሁ የመስተዳደሩ ድራማ እኮ ልማታዊ ሳይሆን ፕሮፓጋንዳዊ ነው - በቃ ደረቅ- ችኮ - “እንጨት እንጨት” የሚል፡፡ የእንካስላንቲያው ግን ሌላው ቢቀር ያዝናናል፡፡ ሌላ ደግሞ ይሄውላችሁ - እንካስላንቲያ? በምንቲያ? በአምሮት! ምን አለህ በአምሮት? ሥልጣን ለሰጠህ ህዝብ ይኑርህ አክብሮት፡፡ አሪፍ መልዕክትና ቁም ነገር ይዛለች አይደል? ማንን እንደሚመለከት መግለፅ ግን አስፈላጊ አይመስለኝም (ግልፅ ነዋ!) እስቲ ደግሞ በመልካም አስተዳደር ዙርያ ደራሲው የፈጠረውን እንካ ስላንቲያ እንይ፡- እንካስላንቲያ? በምንቲያ? በመምጠቅ! ምን አለህ በመምጠቅ? መልካም አስተዳደር እንዳለ ለማወቅ ባለሥልጣን ሳይሆን ሕዝብን ነው መጠየቅ፡፡
ልክ ብሏል! በተለይ ኢቴቪ እቺን ቢሰማ ይጠቅመዋል፡፡ በቃ በልኩ የተሰፋች ናት! ራሱ ኢህአዴግ በ9ኛው ጉባኤ የመልካም አስተዳደር ችግር እንዳለ የተረዳው፣ከህዝቡ ምሬት እንደሆነ በግልፅ ተናግሯል እኮ፡፡ ኢቴቪ ግን ሁሌም ባለስልጣናትን ነው የሚጠይቀው፡፡ ምናልባት ወደፊት ግን ከኢህአዴግ ይማራል ብለን ተስፋ እናደርጋለን (አበሻ ተስፋ አይቆርጥማ!) እኔ የምላችሁ … የሰሞኑ ምርጫ እንዴት ነው? መረጣችሁ ወይስ ተመረጣችሁ? አንዱ ወዳጄ ምን አለኝ መሰላችሁ … “ምርጫ ድሮ ቀረ!” (የፈረደበትን የ97 ምርጫ ማለቱ እኮ ነው) ወዳጄ እርሙን አላወጣ ብሎኝ ነው እንጂ … ነግሬው ነበር እኮ! “እንደዛ ዓይነቱን ምርጫ ኢህአዴግ ዓይኑ እያየ አይደግመውም” ብዬ! (የለየለት ሞኝ አደረገው እንዴ?) ባለፈው ሳምንት የመኢአድ ሊቀመንበር ያሉት ግን ትንሽ ከበድ ይላል፡፡
አሁንም መኢአድ አለ እንዴ? (ይሁና!) እናላችሁ --- ስለምርጫው ተጠይቀው ኢንጂነር ኃይሉ እንዲህ አሉ “ይሄ ምርጫ ሳይሆን ንጥቂያ ነው!” እንዴት ቢማረሩ ነው ባካችሁ! ከምርጫው ራሱን ያገለለው የ33ቱ ፓርቲዎች ቡድን (ስም አልወጣለትም አይደል?) ምን ነበር ያለው? “ኢህአዴግን ለማጀብ ወደምርጫው አንገባም!” ብለው ነበር (ምን ያድርጉ? ምህዳር የለማ!) ባለፈው ሳምንት ከምርጫው በኋላ የምርጫ ቦርድ ሃላፊው ምን አሉ መሰላችሁ? (እኚህ እንኳን ፓርቲዎችን ሁሉ እንደልጆቼ ነው የማየው ያሉት) “እንዳሁኑ ምርጫ ፓርቲዎች ሳይወዛገቡ በሰላም የተጠናቀቀበት ጊዜ የለም” ይሄን የሰማ የቀድሞ የኢህአዴግ ደጋፊ ወዳጄ (አሁን ሃይማኖተኛ ሆኗል) “እውነታቸውን እኮ ነው … በምርጫው አልተሳተፉማ!” ብሎ እርፍ አለ! (ሰው ሁሉ በቀጥታ መናገር ተወ ማለት ነው?) እኔ ደግሞ ያስገረመኝ የአንዳንድ መራጮችና ተመራጮች አስተያየት ነው፡፡
ባለፈው እሁድ አንዱ መራጭ ድምጽ ሰጥቶ ሲወጣ የኢቴቪ ጋዜጠኛ ያገኘውና “ምርጫው እንዴት ነበር?” ይለዋል፡፡ (ኢንተርቪው በጥቆማ ነው የሚባለው ውሸት ነው አይደል?) መራጩም - “የመብራት ችግር አለ፣ የውሃ ችግር አለ፣ የመሰረተ ልማት ችግር አለ፣ በአጠቃላይ ብዙ ችግሮች አሉ፡፡ እነዚህን ችግሮች የሚፈታልኝን መርጫለሁ” (ማንን ይሆን?) ኢቴቪ ያነጋገራቸውን አስተያየት ሰጪዎች እንደኔ በቅጡ ሰምታችኋቸው እንደሆነ አላውቅም፡፡ “የመረጥኩት ኢህአዴግን ነው” ማለት እኮ ነው የሚቀራቸው፡፡ (ነግረውን ቢለይላቸው ይሻል ነበር!) ሌላ መራጭ ደግሞ እንዲህ አለ - በፈረደበት አንድ ለእናቱ ኢቴቪያችን፡፡ “ምርጫው ዲሞክራሲያዊና ፍትሃዊ እንዲሁም ልማታዊ ነው ማለት ይቻላል” አይገርምም… ልማታዊ ምርጫ! ኢህአዴግ ራሱ እኮ ሌላ ሌላውን እንጂ ምርጫውን ልማታዊ ሲል ሰምቼው አላውቅም (አሁን ይጀምር ይሆናል!) አንዱ ጐልማሳ መራጭ ደግሞ አስተያየታቸውን የጀመሩት የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር መለስን በማወደስ ነው፡፡ “የባለራዕዩን መሪ አርአያ ተከትለን…” አሉና እሳቸውም “ይሆነኛል…ይጠቅመኛል” ያሉትን መምረጣቸውን ነገሩን፡፡
አንደኛዋ ወይዘሮ ደግሞ ምን ብትል ጥሩ ነው? “ጫንቃችንን ያቃለለልንን ፓርቲ መርጫለሁ” (ኢህአዴግ ብላ ብትገላገልስ?) ከሁሉም ግን የኢራፓ ሊቀመንበር የሰጡትን አስተያየት የሚያህል የለም (ዊርድ እኮ ነው!) “ዝናብ የለም፤ ደመና ነው፤ ሙቀት የለም…ሁሉ ነገር ኖርማል ነው” (ስለምርጫ እንጂ ስለሜትሮሎጂ ማን ጠየቃቸው?) የሆኖ ሆኖ እስካሁን “የምርጫው ሂደት ዲሞክራሲያዊ፣ ፍትሃዊና ልማታዊ ነው” ተብሏል፡፡ ግን እኮ ድሮም ቢሆን በጥባጩ ህዝብ ሳይሆን ፓርቲዎቹ ናቸው - ገዢው ፓርቲና ተቃዋሚዎቹ! የብጥብጣቸውን ሰበብም አሳምረን እናውቀዋለን - የፈረደበት ሥልጣን ነው!! አሁን ግን የምርጫው ውጤት ቀድሞ የሚታወቅ ስለሆነ (መጨረሻው እንደሚታወቅ ፊልም) ፓርቲዎቹ አልተወዛገቡም (የተሳተፉት ማለቴ ነው!) ለነገሩ ብዙዎቹ ገና የኢህአዴግን ሚሊዮን እጩዎች ሲሰሙ እኮ ነው እጅ የሰጡት (የቤት ሥራቸውን አልሰሩማ!) እነዚህ የጦቢያ ተቃዋሚዎች ግን ሁነኛ መካሪ ሳያስፈልጋቸው አይቀርም (ቢቻል በዲሞክራሲ የዳበረ ልምድ ካላቸው አገራት!) እንዴ…”በምርጫ አንሳተፍም!”፣ “ፓርላማ አንገባም!”፣ “አንደራደርም” ምናምን እየተባለ እስከመቼ ይዘለቃል? እኔ የምጠረጥረው ምን መሰላችሁ? ወይ የፖለቲካ ጨዋታውን አላወቁበትም ወይ ደግሞ ኢህአዴግ አንድ ነገር አስነክቷቸዋል (የምህዳሩ መጥበብ እንዳለ ሆኖ ማለቴ ነው!) እንዴ ቢጠብም እኮ ባለችው ዕድል መንፈራገጥ ነው፡፡ ሽሽትማ ለማን በጀ? እንግዲህ ፖለቲካዊ ወጋችንን በእንካስላንቲያ እንደጀመርነው በእንካስላንቲያ እንቋጨው፡፡ (ለደራሲ ኃይለመለኮት መዋዕል ምስጋናችን ይድረሰው እያልን!) እንካስላንቲያ? በምንቲያ? በቁርቁስ! ምናለህ በቁርቁስ? አንጠርጥረህ ምረጥ ጥሩን ከልክስክስ ለምክር ቤት ምርጫ ዋሾን አታግበስብስ፡፡ (ወንዳታ ብለናል!!)
ኢትዮጵያዊ መልኮች በአሜሪካ
መልክአ ኢትዮጵያ - ፲፬
የቺካጎ ቆይታዬ የመጨረሻዋ ምሽት ላይ ነኝ። በዚህች ምሽት ከፍ ያለ ስምና ዝና ባለው ‹‹ካዲላክ ፓላስ›› (Cadillac Palace) ቴአትር ቤት ከታደሙት በሺሕ ከሚቆጠሩ ተመልካቾች አንዷ ኾኛለኁ። ተውኔቱ ሚልዮኖች በቴአትርና ሲኒማ ቤት ደጃፍ ተሰልፈው ላለፉት ኻያ ስምንት ዓመታት የተመለከቱትና የቪክቶር ሁጎ ድርሰት የኾነው ሌስ ሚዝራብልስ (Les Miserables) ሙዚቃዊ ብሮውዌይ ቴአትር ነው፡፡ የቤቱ አስተናባሪዎች በአክብሮት የሰጡኝን፣ ስለ ተውኔቱና ተዋንያኑ የተሟላ መረጃ የያዘውን የቴአትር ቤቱን ባለቀለም መጽሔት እያገላበጥኩ በተሰጠኝ የወንበር ቁጥር መሠረት ቦታዬን ይዣለኹ፡፡ በቴአትር ቤቱ ውበት የተማረክኹት ገና ከመግቢያው ጀምሮ ነበር፡፡ ከሰማንያ ሰባት ዓመታት በፊት በ12 ሚልዮን ዶላር ወጪ የተገነባው የቺካጎው ‹‹ካዲላክ ቴአትር››÷ አዝናንተው በሚያስቀምጡ፣ ምቾት ባላቸው መቀመጫዎቹ 2400 ተመልካቾችን ክትት ያደርጋል፡፡ ቴአትር ቤቱ በየጊዜው በሚደረግለት እድሳትና የውስጥ ማሻሻያ ዲዛይን ለውጥ ወደር የሌለው የሥነ ሕንጻ ውበት ተላብሷል፡፡ በአዳራሹ ውበት በመመሠጤ የተውኔቱ በሰዓቱ አለመጀመር ብዙም ግድ አልሰጠኝም፡፡ የውስጠኛውን ክፍል ጣሪያ ለማየት ቀና ያደረግኁትን አንገቴን፣ ምን አንገቴን ብቻ ክሣደ ልቡናዬን፣ እዚያው ተክዬው ቀርቻለኹ፡፡
ዲዛይኑ በአንድ ሰው ወይም በአንድ ወቅት የአእምሮ ፈጠራ ውጤት ብቻ መሠራቱ አጠራጣሪ ነው፤ ተጠበውበታል፤ ተጨንቀውበታል፡፡ ስፋቱ፣ የወንበሮቹ አደራደር፣ በመድረኩ ላይ የወረደው መጋረጃ ግርማ ሞገስ ተኩረው፣ ቆፍረው እንዲያዩት ያገብራል፡፡ የተገጣጠሙት ቁሳቁሶችና የተቀባው ቀለም ሕብሩ፣ ሥነ ርእዩ ውብ ነው ከማለት በቀር መግለጫ አጥቼለታለኹ፡፡ ሁሌም በሰው አገር ያየኹትን የሰው ነገር ከማውቀው ጋራ ለማነጻጸር በምናቤ ወደ አገሬ እመለሳለኹ፤ በሐሳቤም እዋቀሳለኹ፡፡ የካዲላክ ፓላስ ቴአትር ሥነ ኪን ባለአንበሳ ሐውልቱን ቴአትር ቤታችንን - ብሔራዊ ቴአትርን - አስታወሰኝ፡፡ በንጽጽሬ ግን ከመዝናናት ይልቅ ከፍተኛ ተግሣጽ እንደደረሰበት አዳጊ ዙሪያ ገባውን እያየኹ ሰውነቴን አሸማቅቄ፣ ድምፄን አጥፍቼ፣ ጥፍሬን እየቆረጠምኹ ‹‹ሌስ ሚዝራብልስ›› የተሰኘውን የብሮድዌይ ተውኔት መጀመር መጠባባቅ ያዝኹ፡፡ የተውኔቱ ታሪክ በፊልምም ተሠርቷል። በአሜሪካ ቦክስ ኦፊስ የሰንጠረዡን የላይ እርከን የተቆናጠጡ ፊልሞችን በትኩስነታቸው የሚያስኮመኩመው ‹‹ኤድናሞል ማቲ ሲኒማ›› ከወራት በፊት ሺሓት በአድናቆት የጎረፉለትን ‹‹ሌስ ሚዝራብልስ›› የተሰኘውን ፊልም አስመጥቶት ነበር፡፡
ፊልሙ በተመሳሳይ ርእስ ለአንባብያን በበቃው በታዋቂው ፈረንሳዊ ደራሲና ጸሐፊ ተውኔት ቪክቶር ሁጎ መጽሐፍ ላይ የተመረኮዘ ነው፡፡ መጽሐፉ ‹‹ምንዱባ›› እና ‹‹መከረኞቹ›› በሚሉ ርእሶች ተተርጉሞ ለአገራችን አንባቢዎች ቀርቧል። በኢትዮጵያ ሬዲዮ የ‹‹ከመጻሕፍት ዓለም›› ፕሮግራም በተተረከበት ወቅት የመጽሐፉ ተወዳጅነት ከፍተኛ ደረጃ ላይ ደርሶ እንደነበር አስታውሳለኹ። ለዓመታዊው የኦስካር ሽልማት በበርካታ ዘርፎች ታጭቶ የነበረውና በሙዚቃዊ ድራማ ዘውግ የተሠራው ፊልሙ በኤድናል ማቲ ሲኒማ ቤት ለመቆየት የታደለው ግን ለአንድ ቀን ብቻ ነበር፡፡ በተመልካች ዘንድ አልተወደደም በሚል የመታያ ጊዜው በአጭሩ ተቀጭቷል፡፡ በኢትዮጵያ እምብዛም ተቀባይነት ያላገኘው ይህ ፊልም፣ በአሜሪካና በተቀረው ዓለም ሚልዮኖች በሲኒማ ቤት ተሰልፈውለታል፡፡ ተውኔቱን ደግሞ በ28 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ወደ 60 ሚልዮን ተመልካች ታድሞበታል፡፡ ለሁለት ሰዓት ከ50 ደቂቃ የታየው ተውኔት ከተጀመረበት እስከተጠናቀቀበት ደቂቃ ድረስ ለቅጽበት እንኳ ሌላ ነገር የማሰቢያ ጊዜ አልሰጠኝም።
የመድረክ ዝግጅቱ፣ ድምፁ፣ ሙዚቃው፣ አልባሳቱ፣ የተዋናያኑ የትወና ብቃት ከኹሉም በላይ ደግሞ የተጠቀሙበት ቴክኖሎጂ እጅግ ይማርካል፡፡ ታሪኩ የሚጠይቃቸው ነገሮች በሙሉ በመድረኩ ላይ በወጉ ተሟልተዋል፡፡ ቤቶቹ፣ መንገዱ፣ ዛፎቹ፣ ድልድዩ፣ ውኃው፣ ጦርነቱ ሳይቀር ልክ እንደ ፊልሙ በተውኔቱ ላይም ተሰናኝተው ታይተዋል፡፡ ቴአትሩ ተጠናቆ ተዋንያኑ ለተመልካቹ እጅ እስኪነሱ ድረስ ጠቅላላ መሰናዶው ለእውንነት የቀረበ፣ በእውኑ ዓለም የሚያቆይ ነበር፡፡ በአዳራሹ የሞላው ተመልካች ከመቀመጫው ተነሥቶ በከፍተኛ ጭብጨባ ለተዋንያኑ አድናቆቱን ገለጸ፡፡ የእኔ አድናቆት ግን ለአገሬ የጥበብ ሰዎች በዘርፉ የተሟላ መሰል ቴክኖሎጂንና ብቃትን አሟልቶ እንዲሰጣቸው ከመመኘት ጋራ ነበር፡፡ አዳራሹን ለቀን ወደ ሆቴላችን በሚያደርሰን አውቶብስ ውስጥ ስንገባ እንደተለመደው ስለውሎአችን ለሚጠይቀን ቡድን መሪው ጆን ሁላችንም በአንድ ላይ፣ ‹‹እጅግ በጣም ያምራል፤ እንዲህ ያለውን ጥበብ፣ ቴክኖሎጂ እንድናይ ስለጋበዛችኹን እናመሰግናለን›› በማለት ምላሽም ልባዊ ምስጋናም አቀረብን፡፡ ወደ ማደሪያችን እስክንደርስ ከቴአትሩና ተውኔቱ ሌላ ወሬ አልነበረንም፡፡ በርግጥም ቴአትሩ፣ ተዋንያኑና ተውኔቱ አፍሪካውያንን እጅግ በጣም አስደንቆንና አስደስቶን ነበር፡፡ ******************
አሜሪካ በመዝናኛ ኢንደስትሪው ላይ ከፍተኛ ትኩረት እንደምታደርግ ካዲላክ ፓላስ ቴአትርና ተውኔቱ ኹነኛ ማሳያ ነው፡፡ ቆየት ብዬ እንደታዘብኹት በየከተሞቿ እንደ ካዲላክና ከዚያም በላይ እጅግ የተጋነነ ውበት ያላቸው ቴአትር ቤቶች አላት፡፡ የኒውክሌርን ያህል ትቆጥራዋለች በሚባለው የፊልሟ ጥበብም ከራሷ አልፎ የዓለምን ቀልብ ስባበታለች። ራሷን ለገበያ የምታቀርበው፣ በሌሎች ዘንድ የምትናፈቅና የምትወደድ እንድትኾን የምታደርገው በፊልም ጥበብ ይመስለኛል፡፡ የአገሪቱ ወጣቶች በብዛት ወደ ሕክምና ሞያ እንዲገቡ ለማድረግ ከፍተኛ በጀት እየተመደበ እንኳ ምርጥ የቴሌቭዥን ተከታታይ ፊልሞች ይሠራሉ፡፡ ከወጣቶቿ የሚበዙት ከዋና ሥራቸው ወይም ሞያቸው ቀጥሎ ትኩረታቸው ለመዝናኛ ወሬ ነው፡፡ ርካሽና ፈጣን የኢንትርኔት ቴክኖሎጂውን አዘውትረው ጆሯቸው ላይ በሚሰኩት ማዳመጫና በስልካቸው ሲከታተሉና መረጃ ሲሰበስቡ ውለው ያድሩበታል፡፡ ከወገኖቻችን እንደ አንዳንዶቹ በምኑም በምኑም ሲያንቧትሩና ሲዳክሩ አይውሉም። የሚመለከታቸውን ነገር ጥንቅቅ አድርገው በጥልቀት ካወቁ ስለተቀረው ጉዳይ እነርሱን አይመለከታቸውም። ለዚህ ዝንባሌያቸው ሚዲያዎቻቸውም ሚና ሳይኖራቸው አይቀርም፡፡
በአንድ አካባቢ ስፍር ቁጥር የሌላቸው የቴሌቭዥን ጣቢያዎች ቢኖሩም ከጥቂቶቹ በስተቀር አብዛኛዎቹ የቶክ ሾውና የመዝናኛ ቻናሎች ናቸው፡፡ ጥቂት የሚባሉት የዜና ቻናሎችም ቢኾኑ ምንም ቢፈጠር ከአካባቢያዊ ጉዳዮች ውጭ ሌላ ነገር አያቀርቡም፡፡ ዜናዎቻቸው በሙሉ ስርጭቱ በሚሸፍነው ግዛት ክልል ስለተከናወኑ ጉዳዮች ብቻ ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር ስለ ዓለም ወሬ መስማት የፈለገ ዓለም አቀፍ ቻናሎችን መግጠም አሊያም በኢንተርኔቱ ማሠሥ ግድ ይለዋል፡፡ ለዚህ ግን ጊዜ ያላቸው አይመስሉም፡፡ ቱሪስቶቹ ሌላ አገር ለመጎብኘት የሚነሡት በጡረታ ጊዜያቸው ላይ ነው። ወጣቶቹ የዕረፍት ጉብኝት ማድረግ የሚጀምሩት በዚያው በአሜሪካ ሌሎች ግዛቶች ነው፡፡ ከአሜሪካ የሚወጡ ወጣቶች ካሉ ጥቂቶች ናቸው፤ እነርሱም የቤተሰቦቻው ፈቃድና ፍላጎት መሠረት ያደርጋሉ፡፡ አሜሪካውያን በቤታቸው የሚያደርጉትን እንግዳ አቀባበልና ኑሯቸውን እንድንመለከት በየተመደብንበት ቤት ለአንድ ቀን ቆይታ አድርገን ነበር፡፡ እኔ፣ ናይጄሪያዋ ቲሚ እና ኬኒያዊው ታሩስ አስማ አንዋር ወደተባለች ወጣት አሜሪካዊት መኖሪያ ቤት ተመራን፡፡
አስማ የዐረብ ዝርያ ካላቸው ቤተሰብ የተወለደች ብትኾንም ተወልዳ ያደገችው ግን አሜሪካ ውስጥ ነው፡፡ በደቡብ ምሥራቅ ኤስያ አገሮች ጋዜጠኛና የንግግር ጸሐፊ ኾና ሠርታለች፡፡ አሁን የሕግ ባለሞያ በመኾኗ ፍሎሪዳ - ፔንሳኮላ ውስጥ በወንጀል መከላከል ጥብቅና ትሠራለች፡፡ ዐሥራ ሦስት የዓለም አገሮችን ተዘዋውራ ጎብኝታለች፤ አፍሪካ ውስጥም ግብጽን ጎብኝታለች፡፡ አስማ ዘንድ የተመደብነው ስለ አፍሪካ ታውቃለች ከሚል እንደኾነ ገምቻለኁ፡፡ እውነትም የአስማ ዓለም አቀፋዊ ዕውቀት ሰፋ ያለ ነው፡፡ ከየት እንደመጣኹ ጠይቃ ‹‹ከኢትዮጵያ›› ስላት ‹‹እርሷ ደሞ የት ነው የምትገኘው?›› ብላ እንደሌሎቹ አላሸማቀቀችኝም፡፡ አገሬን ታውቃታለች፡፡ መቼም ኢትዮጵያውያን ወደ ባሕር ማዶ ሲጓዙ አገራቸው በብዙ መልኩ በዓለም ሕዝብ ፊት ታዋቂ እንደኾነች ያስባሉ፡፡ ጥንታዊቷና የዘመናት ታሪክ ያላት አገራችን የት እንደኾነች መጠየቅ ምን ያህል ግርታ እንደሚፈጥር የሚታወቃቸው ግን ከአገር ሲወጡና መልክአ ምድራዊ መገኛዋን የመጠየቅ ‹ድፍረት› ሲገጥማቸው ነው፡፡ በአንድ አፓርትመንት ውስጥ በሚገኘው የአስማ መኖሪያ አብረናት አመሸን፡፡ ስለ ሥራዋ፣ ኑሮዋ አጫወተችን፡፡
ብዙውን ጊዜ እንደምታደርገው የነገረችንን ፓርቲ መሰል ዝግጅት ለምሽቱ አዘጋጅታለች፡፡ ቀለል ካለ ራት ጋራ ወይን እየተጎነጩ መጨዋወት እንደምትወድ ነገረችን፡፡ በዕለቱም ከተለያዩ ሰዎች ጋራ ብንወያይ እንደማይገደንና እንደማይደብረን በማሰብ በርካታ ጓደኞቿን መጋበዟን ነገረችን፡፡ ራት አዘጋጅታ ስታጠናቅቅ ተጋግዘን አቀራረብነው፡፡ ማምሻውን የተጠሩት ጓደኞቿ መጠጥ እየያዙ በሰዓቱ ተገኙ፡፡ አንድ ወጣት ፕሮፌሰርን ጨምሮ ሁሉም የአስማ ጓደኞች ምሁራን ናቸው፡፡ ከአስማ በቀር አንዳቸውም በስም እንኳ አገሬን አያውቋትም፡፡ ታሪክና ጂኦግራፊ ያበቃ መሰለኝ። ለእነርሱ ኢትዮጵያን ለማስረዳት ያልፈነቀልኁት ደንጊያ የለም፡፡ ሰሚ ባገኝ ብዬ በዝነኛው ቡና መሸጫቸው ውስጥ የሚገኘው የሲዳማ ቡና መገኛ እናት አገር ኢትዮጵያ መኾኗን ተናገርኁ፡፡ ቀደም እንዳልኋችኹ ከአገሬ ስነሣ ኢትዮጵያ የምትባለዋን አገር ዓለም ኹሉ እንደሚያውቃት የነበረኝን ሐሳብ ድራሹን አጠፉብኝ፡፡ ከራት በኋላ በነበረን የሞቀ ጨዋታ ስለ ናይጄሪያ፣ ኢትዮጵያና ኬንያ ለማስረዳትም ጊዜ ወስዶብን ነበር። ሁላችንም በየፊናችን ስለ አገራችን ለማስረዳት እንሻማለን፡፡ በሽሚያችን፣ የናይጄሪያዋ ቲም ወትሮውንም ስታወራ በጣም ትፈጥናለችና ያን ዕለት ስለ አገሯ እየተሽቀዳደመች ስታስረዳ÷ ‹‹እንዴት የሰው አገር ቋንቋ እንዲህ ፈጥነሽ ልታወሪ ቻልሽ?›› ብለው አሸማቀቋት፡፡
የየራሳችን ቋንቋ ያለን ሕዝቦች በእነርሱ ቋንቋ ማውራታችን በራሱ አስገርሟቸዋል፡፡ እኔና ኬንያዊው ጋዜጠኛ ስለየራሳችን አገር ስንገልጽ፣ ‹‹አትሌቶቻችን ከዓለም አንደኛ ናቸው›› በማለታችን የተካረረ ክርክር ተነሥቶ ነበር፡፡ ኬንያዊው ታሩስ በክርክሩ መሀል፣ ‹‹እናንተ ያላችኹ ኀይሌ ገብረ ሥላሴ ብቻ ነው›› ሲል የመምጫዬ አገር ታሪክና ጆግራፊያዊ አቀማመጥ ግራ አጋብቶት የነበረው አንዱ ወጣት አሜሪካዊ፣ ‹‹ገብረ ሥላሴ እናንተ አገር ነው እንዴ?›› ብሎ የመረጃ ክፍተቱን ስላሰፋልኝ ደስ አለኝ፡፡ ይህን ያህል ግዙፍ የመረጃ ክፍተት በማግኘቴም ስለቀሪዎቹ አትሌቶች ኮራ ብዬ አስረዳኹ፡፡ አሜሪካኖቹ የታሪክና ጂኦግራፊ ዕውቀታቸው አነስተኛ ነው፡፡ ይህ የኾነው ደግሞ አይጠቅመንም ብለው ስለሚያስቡ ነው፡፡ እነርሱን የሚጠቅመው የሚመለከታቸውን ጉዳይ አጥብቆ ይዞ ዕውቀታቸውን ማጎልበት፣ በዚያም ላይ መሥራትና በዕረፍት ጊዜያቸው መዝናናት ብቻ ነው፡፡ በእነርሱ አገር የጠቅላላ ዕውቀት የሬዲዮና ቴሌቭዥን ጥያቄና መልስ ውድድር የለም፡፡ በጨዎታችን ያግባባን የጋራ ጉዳይ ቢኖር የአሜሪካ ምርጫና ሙዚቃ ነበር፡፡ ስለ ዘፋኞቻቸው ጠንቅቀው ያውቃሉ፡፡ ይህን ስመለከት ቻርልስ ኦያንጎ የተባለ ዑጋንዳዊ ደራሲና ጋዜጠኛ፣ ‹‹ ቢራና የአውሮፓ እግር ኳስ ባይኖር ኖሮ የአፍሪካ መሪዎችን ምን ይውጣቸው ነበር?›› ያለውን አስታውሼ ‹‹ለመዝናኛው ኢንደስትሪ እንዲህ ትኩረት ባትሰጥ ኖሮ አሜሪካን ምን ይውጣት ነበር?›› ብዬ አሰብኁላት፡፡ አስተሳሰቤ ግን የሞኝነት መኾኑን ቆየት ብዬ ተረዳኁት፡፡ አሜሪካኖች በኹሉም ጉዳዮች ላይ ስለሚመለከታቸው ነገር ለማወቅ የሚቀድማቸው የለም፡፡
የታሪክና የጂኦግራፊው ጉዳይም ከሚመለከታቸው ጋራ ስላልተገናኹ ይኾናል፡፡ ይህን የተረዳኁት ደግሞ የኮንግረስ ሠራተኛውን ማትን ዋሽንግተን ዲሲ ባገኘኁት ጊዜ ነበር፡፡ ወደ ኢትዮጵያ የመመለሻ ጥቂት ቀናት ሲቀሩኝ ሌላ ከተማ በሚኖሩ ጓደኞቼ አማካይነት ያገኘኁት ማት አሜሪካዊ መኾኑን እስክረሳ ድረስ ሐበሻ መስሎኛል፤ ሐበሻ ኾኖብኛል፡፡ ስለ አገሬ የማያውቀው ነገር የለም፡፡ እኔ እንደርሱ አገሬን አላውቃትም ብል አልተሳሳትኁም። ስለ ብዙኀን መገናኛውና ጋዜጠኞቻችን፣ ስለ ፖሊቲካውና ፖሊተከኞቻችን አንዲትም ሳትቀረው ያውቃል፡፡ ስለ ፖሊቲከኞቻችን ማንነት፣ ጠባይዕና የዕውቀት ይዞታ ጨምሮ ጥቃቅን ነገራቸውን ያወራል። በአገር ውስጥና በውጭ አገር የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንን የፖሊቲካ አስተሳሰብና አካሄድ ያውቃል፡፡ ታዋቂዎቹን የተቃውሞ ፖሊቲካ ፓርቲ አመራሮች በስምና በመልክ ለይቶ የሚገኙበትን ቦታና ኹኔታ ጭምር ጠንቅቆ ይናገራል፡፡ ፖሊቲካዊ ጉዳዮችን በሚመለከት በተለያዩ መድረኮች በሚካሄድ ውይይት ላይ የትኛው ፖሊቲከኛ ማስታወሻ እንደሚይዝና ማንኛው ፖለቲከኛ ተኮፍሶ እንደሚያወራ ሳይቀር አጥንቷል፡፡ ስለ ገዥው ፓርቲ ሹማምንትማ በሚገባ ያውቃል፡፡ በኢትዮጵያውያን ሬስቶራንት ጥሬ ክትፎ አብሮኝ የበላው ማት ሻይ ውስጥ ስለምንጨምረው ቀረፋና ቁርንፉድ (ጣዕማችን) ኹሉ ያውቃል፡፡ ስለ ማት ያለኝን ምስክርነት በእኔ የመረጃ ክትትልና የዕውቀት ዳርቻ ለማረጋገጥ ልድፈርና፣ ማት ስለ እኔ አገር ያለውን ዕውቀት ስሰማ አሜሪካውያን ሥራዬ ብለው በሚከታተሉት ጉዳይ ላይ ያላቸውን የመረጃና ዕውቀት መልክና ልክ በወጉ አሳይቶኛል፡፡ (ይቀጥላል)
“ኢህዴግን የመሰለ ፓርቲ በአፍሪካ የለም” አቦይ ስብሃት ነጋ
- ተቃዋሚዎች የፖለቲካ ፓርቲነት ባህሪም፣ ይዘትም፣ ቅርፅም የላቸውም
- አስመራ ያለው ፀሃይ የጠለቀችበት ጠንቀኛ መንግስት ነው
- ከመለስ በኋላ ህወሓት ተቀባይነት አጥቷል የሚባለው ስህተት ነው
የህወኃት መስራች እንዲሁም በአሁኑ ወቅት የኢትዮጵያ አለማቀፍ የሠላምና ልማት ኢንስቲቲዩት ዋና ዳይሬክተር የሆኑት አቦይ ስብሃት ነጋ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ላቀረበላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡
የመለስን ፋውንዴሽን በአዋጅ ማቋቋም ለምን አስፈለገ? የመንግስትን ጣልቃ ገብነት እንዴት ያዩታል? 54ሺ ሰማዕታት እያሉ እንዴት ለአቶ መለስ ብቻ ተለይቶ ፋውንዴሽን ይቋቋማል የሚሉ ወገኖች አሉና የእርሶ ምላሽ ምንድን ነው? በአፍሪካም በሌላም በሰው ስም የተቋቋሙ ፋውንዴሽኖች አሉ፡፡ እንዴት እንደተቋቋሙ አላውቅም፡፡ የመለስ ፋውንዴሽን በመንግስት አዋጅ መቋቋሙ ተገቢ ባይሆን ኖሮ የኛ ሰዎች አያደርጉትም ነበር፡፡ ለመሆኑ የሚከለክል ሕግ አለ ወይ? 54 ሺ ሰማዕታት ምናልባት የትግራይ ሰማእታት ብቻ ነው ሊሆኑ የሚችሉት፡፡ የአሁኒቱ አዲሲቱ ኢትዮጵያ፣ መላ ህዝቦች የጠራ ኢትዮጵያዊ ኘሮግራም ባይኖራቸውም፣ ከዚህ የከፋ የለም በማለት ማእከላይ መንግስትን የተዋጉበት ዘመንና የከፈሉት የንብረትና የህይወት ዋጋ የሚታወቅ ይመስለኛል፡፡
ከዚህ የከፋ ሲኦል የለም ብሎ ያለ ብቁ መሪ ሲፋለም የሞተውም ሰማእት ነው፡፡ ለነዚህ ሰማእታት በየክልሉ መታሰቢያ የተሰራላቸውም እየተሰራላቸውም ያለ ይመስለኛል፡፡ አልተረሱም፡፡ እነዚህ በየክልሉ ያሉ መታሰቢያዎች የመለስም መታሰቢያዎች ናቸው፡፡ የመለስ ፋውንዴሽንም የሁሉ የሃገሪቱ ሰማእታት ፋውንዴሽን ነው፡፡ ነጣጥሎ ማየት ሳይንሳዊም ፍትሃዊም አይደለም፡፡ ሁሉም ሰማእታት መንፈሳዊና ህሊናዊ ግንኙነት አላቸው፡፡ ለመላ የአትዮጵያ ህዝብም ዘልአለማዊ የህዝባዊነት ሃይል መልእክት እያስተላለፉ ይኖራሉ፡፡ አሁን የሚያሰጋው የመለስ ራእይ እንደቁምነገር ሳይሆን እንደመፈክር ይዞ በጥገኝነት ተዘፍቆ የነበረው እንደ መደበቂያ፣ አዲሶች ሊጨማለቁ የፈለጉ ደግሞ እንደ መታወቂያ ይዘው፣ ለአመታት ተዘፍቀንባቸው የነበሩ ችግሮችን እንዳንፈታ፣ እንደመጋረጃ እንዳይጠቀሙበት ነው፡፡ በታሪክ መኖር ባህላችን ነውና፡፡ ኢህአዴግ አንድ ውህድ ፓርቲ መሆን አለበት የሚሉ ሃሳቦች አሉና በእርሶ በኩል ያለው እይታ ምንድን? ኢህአደግ ስሙ እንደሚያመለክተው አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ኘሮግራም ይዞ የተነሳ የፖለቲካ ድርጅት ነው፡፡
የነፃ ገበያ ኢኮኖሚን በልማታዊ መስመር እየመራ በዓለም ደረጃ ተወዳዳሪ የሆነ ካፒታሊዝምን በመላ ኢትዮጵያ ለማስፈን ነው ዓላማው፡፡ ይህ እንደህልም እናየው የነበረና፤ በሌላ አገር ስናየውም ስንቀናበት የነበረ የማንነታችን ታላቅ የእድገት ደረጃ ነው፡፡ በዚህ ህልም የሚመስል ግን ሊፈፀም እንደሚችል ምልክት የታየበት የካፒታሊስት ስርዓት፣ ተጠቃሚ ሆነው በቆራጥነት ሊታገሉ የሚችሉት አርሶ አደሩ፤ አነስተኛው ባለሃብትና አብዮታዊ ምሁራን ናቸው፡፡ እነዚህ አራቱ መደቦች የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መሰረቶች ናቸው፡፡ ልማታዊው ባለሃብትንም እንደቆራጥ አጋር ይወስደዋል፡፡ ይህ መደብ በሂደት ሃላፊነቱን በወሳኝነት እየተረከበ ይሄዳል፡፡ አሁን ግን በጥራትም በብዛትም ደካማ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ ሁኔታ እያለም በካፒታሊዝም ግንባታና ዲሞክራሲን በማስፈን ረገድ ሚና አለው፡፡ በኢትዮጵያ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ /የካፒታሊዝም ስርዓት ግንባታ/ ነቀርሳ የሆነው ጥገኛው ነው፡፡
የጥገኝነት አመለካከት በተግባር የሚገለፀው እጅግ በጣም ብዙ በሆኑ መንገዶችና አግባብ ነው፡፡ እጅግ በጣም የህዝብ፣ የሃገር ጠላት ተደርጐ ነው መወሰድ ያለበት፡፡ የጥገኝነት አመለካከትና ተግባር በባለስልጣን ይሁን በባለ ሀብት፤ አገር በመበታተን አይን ቢታይ ከውጭ ወራሪ የባሰ ነው፡፡ ስለዚህ አደረጃጀቱ በግንባር ይሁን በውህድነት፤ የሚለው የመልክ ለውጥ እንጂ የአሰላለፍና፤ የፖለቲካ ይዘቱን አይቀይረውም፡፡ ጉዳዩ በጉባኤው ተነስቶ ይጠናል ተብሏል፡፡ ዋናው ጥያቄ መሆን ያለበት ግን የአብዮቱ ሃይሎች በመሉ በኘሮግራሙ ዙርያ ፀረ ጥገኝነት ማሰለፉና ጥገኝነትን መቆጣጠሩ ነው፡፡ እግረ መንገድ በኘሮግራም ደረጃ የኢህአዴግን የመሰለ የጠራና የወቅቱን የሃገር የእድገት ችግሮች የሚፈታ ኘሮግራም ያለው ፓርቲ በአፍሪካ የለም፡፡
በፓርቲ ብቻ ሳይሆን በመንግስት ባህሪ ደረጃም ኢህአዴግ ተወዳዳሪ የለውም፡፡ የዚህን ብርቅና የላቀ ድርጅት፣ የአደረጃጀት መልክ ከማየት በፊት፣ ኘሮግራሙን ማወቅና ለተፈፃሚነቱ ቅድሚያ መስጠት ይሻላል፡፡ ከአቶ መለስ ህልፈት በኋላ ህወሓት በትግራይ ህዝብ ያለው ተቀባይነት ቀንሷል የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ ብዙ የህዝብ እሮሮ እና የመልካም አስተዳደር እጦት በትግራይ ውስጥ ይታያል ይባላል፡፡ በክልሉ ባለው የስራ አጥነት ችግርም በርካቶች ወደ አዲስ አበባ እየተሰደዱ እንደሆነም ይነገራል፡፡ እርስዎ ምን ይላሉ? በትግራይ የተሰሩ በጐ ነገሮች አሉ፡፡ ግን እንደሌላው ክልል ስራ አጥነት፤የመልካም አስተዳደር እጦትና ሌሎች የጥገኝነት መገለጫዎች ድሮ መለስ እያለም ነበሩ፡፡ ከመለስ በኋላ አዲስ የመጡ ችግሮች አይደሉም፡፡ የህወሓት ኘሮግራም ብቁና በመሰረቱ የማይቀየር ነው፡፡ ድርጅቱ ከመለስ በኋላ ተቀባይነት አጥቷል የሚል አባባል ስህተት ነው፡፡ መጠናከር ግን ያስፈልገዋል፡፡ የመጠናከር ኘሮግራም በህወሓት በየወቅቱ እንደአስፈላጊነቱ የሚመጣ ኦፊሴላዊ ኘሮጀክት ነበር፡፡ ህወሓት እጅግ በጣም ታሪካዊ ድርጅት ስለሆነ፣ በይሉኝታ ምክንያት ድክመትን ደብቆ አድበስብሶ ማለፍ ባህሉ አይደለም፡፡ ከመጠናከር፤ ከመታደስ የሚያፈገፍግ ድርጅት አይደለም፡፡ በየወቅቱ አስፈላጊው ዋጋ እየተከፈለበት የመጣ ህዝባዊ ድርጅት ነው፡፡ ድሮም አሁንም የጥንካሬ ምንጩ አባላቱና ህዝቡ ናቸው፡፡
የህውሓት ከፍተኛ አመራር ውስጥ ባልና ሚስት በርከት እያሉ መሆናቸው “የቤተሰብ ፓርቲ” ያስብለዋል የሚሉ አሉ፡፡ ቀደም ሲል አቶ መለስ እና ባለቤታቸው፤ አሁን ደግሞ አቶ አባይ ወልዱና ባለቤታቸው የስራ አስፈፃሚ ቦታ ላይ መቀመጣቸውን መነሻ በማድረግ በዚህ ቅሬታ የገባቸው አካላት ህወሓት እያከተመለት ነው ይላሉ … ባለፉት ጉባኤዎች አምስት ባልና ሚስት በህወሓት ከፍተኛ አመራር ነበሩ፡፡ አሁን ያሉት ባልና ሚስት ሁለት ናቸው፡፡ “በርከት ብለዋል” የሚለው ጥያቄ ከየት እንደሚመጣ ለኔም ለሌላም የሚገባው አይመስለኝም፡፡ የአሁኑ ጥንዶች ለስራው ብቁ ታጋዮች ናቸው፡፡ ግን ደግሞ ብቃት ተነፃፃሪ ነው፡፡ ስለዚህ አልጠየከኝም እንጂ እኔ በበኩሌ (በግሌ) እነዚህ ሁለቱም ሆኑ ሌሎች ሳይተኩ የቀሩ (ጥቂቶች) ጭምር አሁን በወጡትና በሌላ አዲሶች መተካት ነበረባቸው፡፡ ግን ከፍተኛው የህወሓት አካል ጉባኤው፤ ስለመረጣቸው መቀበል ነው ያለብን፡፡
ብዙ ነገር አያጐድልም፡፡ የኢትዮጵያና ኤርትራ የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ወዴት የሚያመራ ይመስልዎታል? ህዝብ ከህዝብ የሚያጣላ፣ ህዝብን የሚፈራ ፀረ - ህዝብ የሆነ መንግስት ብቻ ነው፡፡ ህዝቦች የሚያፋቅር እንጂ የሚያጣላ ጥያቄ የላቸውም፡፡ በኢትዮጵያና በኤርትራ ህዝቦች አለመተማመን ካለ፣ ድሮ አዲስ አበባ የነበሩ መንግስታትና አሁን ደግሞ (ከነሱ የባሰ) አስመራ ያለው መንግስት የፈጠሩት ነው፡፡ በኢህአዴግ ዘመንም ቢሆን በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ጊዜ በኢትዮጵያ የበላይነት ይዞ የነበረው፣ ከወላጆቹ የማይተናነስ የቀኝ ዘመም አርበኝነት/ ultra rightist patriotism/ አብሶት፣ የሰላም መፍትሄ ዕድል አልሰጥም ብሎ አስመራ ካልደረስኩ፣ አሰብን ካልያዝኩ ብሎ ነበር፡፡ ይህ አይነት አርበኝነት አሁን በኢትዮጵያ የለም፡፡ አሁን በኢትዮጵያ ያለው ሃይል ህዝባዊና የሰላም ሃይል ነው፡፡ በርግጥ የኤርትራ ህዝብ ወንድም ህዝብ ነው ከሚል “አሰብ የኛ ነው” የሚል ጨርሶ ጠፍቷል ማለት አይደለም፡፡ ግን የተዳከመና ጊዜው ያለፈ ነው፡፡ ስለዚህ እንዳልኩት አስመራ ያለው ሃይል ፀሃይ የጠለቀችበት ጠንቀኛ መንግስት ነው፡፡
የኤርትራ ህዝብ ከዚህ ዓይነት ስርዓት ከተገላገለ፣ ኤርትራ ነፃነትዋን ይዛ ከኢትዮጵያ ጋር በጣም የጠበቀና ልዩ ግንኙነት የምታደርግበት ጊዜ ሩቅ አይደለም፡፡ ይህን የተዳፈነና የታመቀ የሁለቱን ህዝቦች ሃይል የሚያቆመው ምንም ነገር የለም፡፡ እኛ ከአካኪ ዘራፍ እንደተገላገልነው ሁሉ የኤርትራ ህዝብም መገላገሉ የማይቀር ነው፡፡ ይህ መሬት፣ ይህ ዳገት፣ ይህ ወንዝ … የሚባለው በህዝቦች ወንድማማችነት መተካቱን ሊያቆመው የሚችል ሃይል ያለ አይመስለኝም፡፡ ስለዚህ ከሌሎች ጐረቤት ህዝቦች በፊት በሁለቱ ህዝቦች መካከል ልዩ ግንኙነት ይፈጠራል፡፡ ቀስ በቀስ እየተሸረሸረ ነው ስለሚባለው የሀገሪቱ የፕሬስ ነፃነት ምን ይላሉ? ቀስ በቀስ እየተሸረሸረ ነው ከተባለ ወደ ሃያ ዓመት ይጠጋል፡፡ ግን እስካሁን ለምን ተሸርሽሮ አላለቀም? አሁን ያለው የግል ኘሬስ ባብዛኛው ፤አንዳንዶቹ እየተሻሻለ ነው ቢሉም፤ እኔ አልፎ አልፎ እንደማየው ግን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ በሃይማኖትም ሆነ በሌላ … ወገን ከወገን የሚያጣላ፤ ለአመፅ የሚሰብክ፤ ስለ ኢህአዴግ መጥፎ ነገር እንጂ ስለሃገሪቱ መሰረታዊ፤ ታሪካዊና ባህላዊ ጉዳዮችና ሌሎች ማነቆዎች ብዙም የማያነሳ ነው፡፡ ከፓርቲ ጉዳይ ባሻገር ስለሃገራዊ ግንባታ ጉዳይ ብዙም ደንታ ያለው አይደለም፡፡
ስለ ሃይማኖት መቻቻል፤ ከታሪካችን የወረስናቸውና የእድገት ማነቆ ስለ ሆኑት ጠባብነት ፤ትምክህት፤ታታሪነት፤ባለሞያነት ወዘተ አይፃፍም፡፡ ባጭሩ መሰረታዊ የሆኑ ያገር ግንባታ ጉዳዮች የማይታይበት፤ ከዚህ አለፍ ብሎም ስለግለሰቦችና ስለአመፅ ወይም ደህና ከተባለ ስለኢህአዴግ መጥፎነት የሚጽፍ ነው፡፡ የሌሎች የአፍሪካ አገሮች የግል ኘሬስና የኛን ስናወዳድረው ፤ እነሱ የሌሎች አገርን ማእከል አድርገው ነው የሚፅፉት፡፡ ሃገራዊ ጥቅም ያስቀድማሉ፡፡ የኛ የግል ኘሬስ ደረጃው በጣም ዝቅተኛ ነው፡፡ ይህ የሞያና የሃገራዊ አመለካከት ደካማነት ካለፈው ስርዓት የወረስነው ነው፡፡ የተከለከለ ስለነበር አልለመድንም፡፡ ለመብቃት ደግሞ ጊዜ ወሰደብን፡፡ ባጭሩ ግን በኔ እምነት፤ በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ዓመፅን የሚሰብኩ ሁሉ፤ ሃገራዊ ክህደት ስለሆነ አደጋ አያመጡም እየተባሉ በቸልተኝነት ማየት ተገቢ አይደለም፡፡ ፖለቲካዊ ኘሮግራሙ የሆነ ይሁን ህገ መንግስቱን መሰረት በማድረግ ለሚካሄደው የሃገር ግንባታ እንከን የሚፈጥር የግል ኘሬስና ፀሃፊዎችን መታገስ አይገባም፡፡ ኢህአዴግ ያለ ጠንካራ ተፎካካሪ በምርጫ መሳተፉ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ግንባታ ላይ ያለው ተጽእኖ ምንድነው? ኢህአዴግ “ጠንካራ ተቃዋሚ” የለም ይላል፡፡?ኢትዮጵያ ውስጥ አስተዋይና ጠንካራ ተቃዋሚ ፓርቲ የመገንባትና የመምራት አቅም ያለው ዜጋ ጠፍቶ ነው ወይስ በኢህአዴግ ጫና ሳቢያ ነው? የኢህአዴግ ሚና በዚህ ረገድ ምን መሆን አለበት? አሁን በኢትዮጵያ ያሉ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች፤ ምናልባት አንድ ወይም ሁለት ይገኙ እንደሆነ እንጂ፤ በፓርቲ ምንነት አንፃር ካየናቸው ፤ የፖለቲካ ፓርቲነት ባህሪም ይዘትም ቅርፅም የላቸውም፡፡
አንድ ፓርቲ የሚገነባው ፖለቲካዊ ስርዓት በጥራት አስቀምጦ፤ የዚህ ስርዓት ሞተር ናቸው የሚባሉትን መደቦች፤ወይም መደብ ወይም የህብረተሰብ ክፍሎች ለይቶ በማስቀመጥና ከዚህ መደብ ወይም ወገን ጋር የጠበቀ ግንኙነት በማድረግ ነው፡፡ የኛ ተቃዋሚዎች በኢህአዴግ ጠላትነት ብቻ ነው የተሰለፉት፡፡ ወዳጃቸውን፣ ወገናቸውን፣ መሰረታቸውን፤ ሳይለዩ ጠላት ብቻ ያስቀመጡ ሰዎች (ቡድኖች) በየትኛው መለኪያ የተቃዋሚ ፓርቲ ስም ይሰጣቸዋል?ለምንገነባው ስርዓት ወዳጅ፤ ጠላት/ተቀናቃኝ/ ብሎ በመፈረጅ ነው ትግሉ መጀመር ያለበት፡፡ የሚገነቡት ስርዓት ምንድነው? የሚገነቡት ስርዓት ተቃናቃኝ ማነው? ተሰላፊ ወዳጅስ ማነው? የትኛው መደብ ወይ የትኞቹ መደቦች ናቸው ወዳጆች ?ባጭሩ በኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ውስጥ የሚጠራቀሙት የተለያየ ቅሬታና ፍላጐት ያላቸው፣ በመሰረታዊ አመለካከት የማይገናኙ ግለሰቦች ናቸው፡ የኔ ጥያቄ ሁኔታቸው በሂደት እየመነመነም ቢሆንም ለምን ይህን ያህል ጊዜ በሚያሳዝን ሁኔታ ቆዩ የሚለው ነው፡፡ እኔ ለዚህ ጥያቄ ያሉኝ መልሶች ሶስት ናቸው፡፡ አንዱ በኢህአዴግ ውስጥ ያለ የጥገኝነት አመለካከትና ተግባር የሚያስጐመጃቸው ይመስለኛል፡፡ ስልጣን ብንይዝ በወገን የመስራት፤የመስረቅ ወዘተ ወዘተ እድል ይኖረናል ከሚል ያለአግባብ የሚያበለፅግ ወንበርን አሻግሮ የማየት ጉዳይ ነው፡፡ ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ በኢትዮጵያ የመጣ ይምጣ፣ ሸምጥጦ መብላት፤ በወገን ለወገን አለአግባብ መስራት፤ ፍርድ ማዛባት የለም ብሎ ኢህአዴግ ደረቅ የስራና የልፋት፤ የህዝባዊ ውጤት ወንበር ብቻ ያሳያቸው፡፡
ሁለተኛ በህዝቡ በተለይ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መሰረት በሆኑ መደቦች፤ የጥገኝነት አመለካከትና ተግባርን በቅፅበት የሚያቃጥል እሳት መለኮስ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ አሁን ያሉት ተቃዋሚ ፓርቲዎች እሳት ይበላቸውና፣ ሕብረ ብሄር ልማታዊ ፓርቲ፤ ባለሃብቱና ላብ አደሩ በየፈርጃቸው እየተደራጁ፣ ቀስ በቀስ እያደጉ ወደ ስልጣን ይጓዛሉ፡፡ በመርህ ደረጃ የኢህአዴግ ዓላማም ፍላጐትም ይህ ነው፡፡ አሁን ያሉ ወንድሞቻችንና ጓደኞቻችን የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች፤ ከኤምባሲ ወደ ኤምባሲ ከመንከራተትና ከውርደት ይገላገላሉ፡፡ ሶስተኛ መፍትሄ፤ የምርጫ ቦርድ ስለፓርቲ ምንነት አጥንቶ፣ ደረጃውን የጠበቀ የፓርቲ መስፈርት ቢያወጣና ቢያስተካክል ሁሉም ወደየስራቸው ይገባሉ፡፡ በነገራችን ላይ በዓለም ላይ ከጥይት፣ ከዱላ፣ ከግድያ፣ ከእስራት… ውጭ በዲሞክራሲያዊ አግባብ ያደገ ካፒታሊዝም የለም፡፡ እንደነሱ እንሁን ማለቴ ግን አይደለም፡፡ በአገሪቱ የተለያዩ ክልሎች እየተፈጠረ ያለው የብሔር መፈናቀል፣ ብሔር ተኮር የሆነው የአገሪቱ ፌዴራሊዝም ውጤት ነው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ እርሶ ምን ይላሉ? በአንዳንድ ክልሎች ውስጥ የሚደረገው መፈናቀል ከፌደራሊዝም ጋር ግንኙነት ያለው አይመስለኝም፡፡ ጉዳዮቹን በዝርዝር አላውቃቸውም፡፡ መንስኤው ግን ሁለቱ ክልሎች ትኩረት ሰጥተው አለማየታቸው ይመስለኛል፡፡ መንስኤው ይህም ይሁን ሌላ በምንም ዓይነት መልኩ መሆን ያልነበረባቸው መጥፎ አጋጣሚዎች ናቸው፡፡ የሆኖ ሆኖ መንግስት እርምጃ እየወሰደ ያለ ይመስለኛል፡፡
ከእንግዲህ ወዲህ የሚያጋጥም አይመስለኝም፡፡ የኢህአዴግ አንጋፋ መሪዎች በአዳዲሶች እየተተኩ ነው፡፡ ይሄ መተካካት አንጋፋዎቹ ላይ የፓርቲ ህልውና ስጋት ይፈጥርባቸው ይሆን? መተካካት በፊት የነበረና አሁንም ያለ ባህርያዊ ጉዞ ነው፡፡ ኢህአዴግ መሰረቴ ካላቸው መደቦች ውስጥ በትግል ተወልዶ በትግል እያደገ፤ በህዝብ ፊት ውጤት እያስመዘገቡ ለሚመጡ ካድሬዎች አመራርን እየተኩ እንዲሄዱ የሚያስችል አሰራር አለው፡፡ ላስቀረው ልወርውረው ብለህ እንደፈለክህ ልታደርገው የማትችል ሃይል ገንፍሎ ከታች ቢመጣ በአስተዳደራዊ እርምጃ ሳይሆን በሂደት የሚመጣ ሃይል ነው ተኪ የሚሆነው፡፡ ስለዚህ ተኪ ሃይል በተደራጀ ሂደት እንጂ በጓዳ አይፈጠርም ማለቴ ነው፡፡ በዚህ ሂደት ከአምናው አመራር የዘንድሮው አመራር የሚበልጥ እንደሚሆን አያጠራጥርም፡፡ ከዘንድሮም አመራር የነገው የበለጠ እየሆነ ይሄዳል፡፡ ምክንያቱም ካለፈው ትግል ቀጣዩ ትግል ነው ከባድና ረቂቅ የሚሆነው፡፡ ከራሱ የበለጠ የአመራር አካል የማይፈጥር አመራር ሲመራ አልነበረም ማለት ነው፡፡
ጨረታ ሲገመግም ነበር ማለት ነው እንጂ ሲመራና ሰው ሲያፈራ አልነበረም ማለት ነው፡፡ አሁን ያልካቸው የተተኩ አንጋፋ አመራር የሚሰጋቸው ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ ላመኑበት ፖለቲካዊ ኘሮግራም በፅኑ እምነት የተሰለፉ ስለነበሩና አሁን በዚያኛው ፅናት ስለሚያምኑበት፣ ድርጅቱ በፈቀደው በሌላ መንገድና አግባብ ትግሉን እንደሚቀጥሉበት ያምናሉ፡፡ በእምነት ተገቢው ግለት የሌላቸው አንዳንድ አንጋፋዎች ካሉም /ያሉም አይመስለኝም/ ለማንኛውም የድርጅት ድክመት ተጠያቂ ስለሚሆኑ ተጠያቂነታቸው ይገፋፋቸዋል፡፡ ስለዚህ የሚያሰጋቸው ነገር ፍፁም የለም፡፡ ለነገሩ አንጋፋዎቹ ወኔያቸው ስለማያስተኛቸው ነው እንጂ፣ አዲሱም አመራር የተለመደውን ድርጅት የማጠናከር ኘሮጀክቱን ቀርፆ፣ የማያሰጋ ሁኔታ ራሱ ይፈጥራል፡፡ የአንጋፋ መሰለፍ ተጨማሪ ነው፡፡