Administrator

Administrator

በአፍሪካ  የነዳጅና ቅባቶች ሥርጭትና ግብይት፣ ግንባር ቀደም የሆነው የሊቢያ ኦይል ግሩፕ፤ ሰፊውን የፓን አፍሪካ የችርቻሮ (ሪቴይል) መሸጫዎችና የነዳጅ ምርቶች መሸጫ አውታረ መረቡን አዲስ ብራንድ ይፋ አደረገ፡፡

ኢትዮጵያን ጨምሮ በ17 የአፍሪካ አገራት በነዳጅና ቅባቶች ሥርጭት፣ በመኪና እጥበት እንዲሁም በካፌ አገልግሎት የሚታወቀው ኦላ ኢነርጂ፤ አዲስ ብራንዱን ያስተዋወቀው በዛሬው ዕለት አመሻሽ ላይ በስካይ ላይት ሆቴል ባዘጋጀው መርሃግብር ላይ ነው፡፡

የኦላ ኢነርጂ ዋና ሥራ አስኪያጅ በመርሃግብሩ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ “ይህ አዲስ ብራንድ እንደ ዘመናዊ የኢነርጂ ተዋናይ በዓለማቀፍ አሻራችን ላይ የኩባንያችንን መለያ/መታወቂያ ይይዛል፤ጥንካሬያችንንና ስኬታችንን ይገልጻል፤እናም በዚህ ዝግ ባለው የለውጥ ምዕራፍ በመላው ግሩፕ ውስጥ ተሰምቶን የነበረውን ተነሳሽነትና ምኞት ይገልጻል፡፡“ ብለዋል፡፡



አዲሱ ብራንድ በ13 አገራት፡- ኒጀር፣ ማሊ፣ ጋቦን፣ ሪዩንዮን ደሴት፣ ቡርኪናፋሶ፣ ካሜሩን፣ ኮትዲቯር፣ግብፅ፣ ኬንያ፣ ኡጋንዳ፣ ሞሮኮ፣ ሴኔጋልና ቱኒዝያ መተግበሩ ታውቋል፡፡

 በዓለማችን ከ70 በላይ አገራት ምርቶቹን በስፋት የሚያቀርበው ቴክኖ ሞባይል፣ ካሞን 20 የተባለውንና የአለም አቀፍ ሽልማት አሸናፊ የሆነውን ዘመናዊ ሞዴል ስልክ ለኢትዮጵያ ገበያ አቀረበ፡፡
በአያት ሬጀንሲ ትናንት ማምሻውን በተካሄደ ስነስርዓት አዲሱ ካሞን 20 ሞዴል ዘመናዊ ስልክ ለኢትዮጵያ ገበያ መቅረቡ ይፋ ተደርጓል፡፡
የኩባንያው የስራ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ለአገራችን ገበያ መቅረቡ ይፋ የተደረገው (Camon 20) ሞዴል ስልክ፤ በ108 ሜጋፒክሰል ካሜራ ፎቶና ቪዲዮ በጥራት በየትኛውም እንቅስቃሴ ውስጥ ሆኖ ለማንሳት ያስችላል የተባለ ሲሆን፤ ይሄው ዘመናዊ ስልክ ተጠቃሚዎች በፍጥነትና በምቾት ዘመናዊ አገልግሎቶችን ሁሉ ለማግኘት እንዲችሉ ያደርጋቸዋልም ተብሏል፡፡
አዲሱ ካሞን 20 ሞዴል ስልክ ለቴክኖ ሞባይልና በአጠቃላይ በአፍሪካ የሞባይል ኢንዱስትሪ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው መሆኑንና ኩባንያው የደንበኞቹን ፍላጎት ለማርካት ሌት ተቀን የሚሰራ መሆኑን ማሳያ ምስክር ነው ያሉት የኩንያው የስራ ሃላፊዎች፤ ከተጠቃሚዎች የሚመጣውን ምላሽ ለመስማት ጓጉተናል ብለዋል፡፡
አዲሱን ካሞን 20 ሞዴል የማስተዋወቅ አካል የሆነውና በተለይም የቴክኖሎጂንና የፋሽንን ጥምረት አዋህዶ መተግበሪያ ማሳየትን አላማው ያደረገ ልዩ የፋሽን ትርኢትም በዚሁ የአዲሱን ሞዴል ሞባይ ስልክ የማስተዋወቅያ ፕሮግራም ላይ ተካሂዷል፡፡
ኩባንያው በአዲስ አበባ ከተማ ጎሮ የሚገኘው የኢትዮ አይሲቲ ፓርክ ውስጥ ያስገነባውን ለአገራችን የመጀመሪያ የሆነው ዘመናዊ ፋብሪካ ውስጥ የተለያዩ አይነትና ሞዴል ያላቸውን የቴክኖ ሞባይል ምርቶችን በመገጣጠም ለገበያ ሲያቀርብ መቆየቱ ይታወቃል፡፡


 መንግስትን፤ ሥራህን በአግባቡ ሥራ እንበለው!


      ይህ የአቶ ሞሼ ፅሑፍ ነው:: የተፃፈው ከዛሬ ሶስት ዓመት በፈት ነው:: ትላንት ኖት ፓዴ ላይ አገኝቼው አነበብኩት :: ፅሑፋቸው በአጠቃላይ በወቅቱ ኢትዮጵያ የገጠማትን ፈታኝ የፖለቲካ ሂደት ተመልክተው የፃፉት ነው:: ስጋታቸውንና መንግስት በቅድሚያ ለምን የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ማክበርና መጠበቅ እንደሚገባው አጥብቀው ያሳስባሎ:: ግና መንግሥት ሞሼና መሰል ኢትዮጵያውያን በወቅቱ የተናገሩት ስጋን  ሆን ብሎ ባለመስማት፣ ዛሬም የሕዝቡ ህይወት አደጋ ላይ ነው:: ኢትዮጵያውያን በየቀኑ በተለያዩ መልኩ ዛሬም እየሞቱ ነው:: እገታው  ግድያው: ..... ዛሬ ከአዲስ አበባ ወጥቶ በሰላም መግባት አይቻልም:: መንግሥት ትንሿን ሃላፊነት መወጣት አልቻለም:: በመላው የሃገሪቱ ክልሎች ዛሬ መንግሥት ያለ  አይመስልም:: እስቲ የአቶ ሞሼን የማሳሰቢያ ፅሁፍ እነሆ!!!
“ዛሬ ላይ የሃይል ሚዛን አሰላለፉ ተለውጧል። ስለ ለውጡ ከምናየውና ከምንሰማው ብቻ ተነስተን ተስፋ ሳንቆርጥ እንዲሻሻል አየመከርን እየወቀስን እንገኛለን። ለውጡ በተሻለ መንገድ እንዲሄድ መታገላችንን ቀጥለናል። ተስፋችንን ትርጉም እያሳጣው የመጣው ነገር፣ በዚህ ዓይነት መቋጫ የሌለው ትርምስ ወስጥ የምንቀጥለው እስከ መቼ ድረስ ነው? ለሚለው ፈታኝ ጥያቄ መልስ አለማግኘታችን ነው። ከቀን ወደ ቀን ከመሻሻል ይልቅ በቀቢጸ ተስፋ ውስጥ መዳከራችን መቀጠሉ አሳሳቢ ጉዳይ ነው።
በዚህ ላይ የማይታረም፣ የማይገሰጽና የማይወቀስ መንግስት ሊጭኑብን የሚዳዳቸው የደምና የአጥንት ፖለቲከኞች ዓይን አውጣነትና አሸማቃቂነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መምጣቱ ስጋቱን እያባባሰው ይገኛል። ባለፉት ሶስት ዓመታት ውስጥ የተከሰቱት ምስቅልቅሎች ያጫሩት ተስፋ መቁረጥና ጣት መጠቋቆሞች እንደተጠበቁ ሆነው፣ ሰሞኑን ከደምቢዶሎው እገታ፣ ከሃይማኖት ተቋማት መቃጠልና ከጥምቀት በአል ጋር በተገናኘ ከተፈጠሩት ግጭቶች በኋላ ግልጽ ሆኖ የመጣው ነገር፣ እነዚህ ሃይሎች የሚደግፉትና ወገኔ የሚሉት ቡድን ስልጣን ላይ እሰከ ቆየ ድረስ አገር ቢጠበስና ሕዝብ ቢቆላ ግድ የሌላችው መሆኑ ነው። ይህ ደግሞ እንደ ሃገርም ሆነ እንደ ሕዝብ በአሳሳቢነትና በትኩረት መታየት ያለበት ጉዳይ ነው።
ልጃገረዶችና ወጣቶች ከሃምሳ ቀን በላይ መታገት፣ የእናትና የአባቶች ሰቆቃ፣ ለቅሶና ዋይታ፣ ሃይማኖታዊ በዓልን በሰላም ማከብር አለመቻል። የሃይማኖት ተቋማት መቃጠል። የዜጎች ስደት፣ መፈናቀል፣ በገጀራ ተደብድቦ፣ በእሳት ተለብልቦ፣ በድንጋይ ተወግሮ፣ ከፎቅ ተወርውሮ መሞትና በርካት ኢኮኖሚያዊ ምስቅልቅሎቻችን መንግስትንና ተቋማቱን ካላስጨነቀ፣ ካላስቆጣ፣ አፋጣኝና የማያዳግም መፍትሔ ለመስጠት መንግስትን በቁርጠኝነት እንዲተጋ ካላደረገው፣ የመንግስት ሚና ከሞት አርጂነት፣ ከለቅሶ ደራሽነትና ከሙት ቀባሪነት ውጭ ምን ሊሆን እንደሚችል እነዚህ ሃይሎች  ቢያስረዱን መልካም ነበር።
እርግጥ ነው እድሜ ሀገራችን ለተቀረቀረችበት የተካረረ፣ አግላይ የብሔር ፖለቲካ፣ ፖለቲከኞቻችንና አክቲቪስቶቻችን ለሕግ፣ ለመርህና ለሞራል ከመቆም ይልቅ ለክልሌና ለወንዜ ልጅ በሚል ምክንያታዊነት የጎደለው የመሞዳሞድ ቅርቃር ውስጥ ተሰንቅረው፣ ጣታቸውንና አንገታቸውን አያወዛወዙ ሲዳክሩ ማየት የተለመደ ነው። በየዘመኑም ደጋግሞ የጎበኘን ትዕይንት ስለሆነ ለዚህ ዓይነቱ ስሜት አዲስ አይደለንም። ነገር ግን የዚህ እሳቤ ችግሩ፣ ለውጡ የተፈለገው የተካረረ የብሔር ፖለቲካን ልክፍት ከጫንቃችን ለማውረድ አንደነበረ መረሳቱ ነው። “የብሔር ጭቆና ተረት” ነው ከሚለው ጀምሮ እስከ “ኦሮማራ” ብዙ መዝሙር ተዘምሮ ነበር።
ቆም ብለን የጋራ ሃገር እንደ ፈጠረ ሕዝብ ልናስብ ይገባል። መታወቅ ያለበት፣ በዳቦ ስም ብልጽግናን ወይም እናትና አባቱ ባወጡለት ስም ኢህአዴግ የሚባለው ግንባር ወደ ስልጣን የመጣው “እባክህን መንግስት ሁንልን“ ተብሎ በፍቃዳችን አይደለም። “ምርጫ አጭበርብረሃል፣ ኮሮጆ ገልብጠሃል“ ተብሎ በገሃድ እየታማና እየተወገዘ እንደነበር አይዘነጋም።
በዚህ መልኩ፣ በዲፋክቶ መንገድ ወደ ስልጣን የመጣ ሃይል ተለውጫለሁ ሲል፣ ቢያንስ ቢያንስ ሕገ መንግስትን፣ ሕግንና ስርዓትን ማስከበር፣ ለተገፉና ለተበደሉ ዘብ መቆም፣ ፍትሕና ርትዕን መዋጀት ከሚጠበቅበት መሰረታዊ ፋይዳ ውስጥ ቀዳሚዎቹ ናቸው። ሕዝብን መፍራትና ማክበር፣ ለሕዝብ ጥያቄ ጆሮ መስጠት ደግሞ ሌላው መርሁ መሆን ነበረበት። ይህ ደግሞ ሕዝብ ፊት ቆሞ ቃለ መሃል የፈጸመበት ትንሹ ግዴታው ነው።
ወገንተኝነትና ድጋፍ አንድ ነገር ነው፣ መራራ ቢሆንም ሃቁን መቀበልና ለመታረም መዘጋጀት ደግሞ ፍትሐዊና የሚያዛልቀው መንገድ ነው። የኛ መንግስት ነው በሚል እሳቤ፣ መንግስትን ከተግባሩ ማዘናጋትም ሆነ “ማባለግ” ተገቢ አይደለም። መንግስትን “የሹም ዶሮ ነው እሽ አትበሉት“ ማለት ውጤቱ ምን ሊሆን አንደሚችል ካለፉት ስርዓቶች በቂ ትምህርት ወሰደናል። መንግስትን፤ ስራህን በአግባቡ ስራ ይባል፣ ግዴታውን ይወቅ።  እንኳን ዛሬ ትናንትም ሥልጣን ርስት አልነበረም።”

 “ወጣ ፍቅር ወጣ” በተሰኘው የመጀመሪያ ነጠላ ዜማው በአጭር ጊዜ ውስጥ ተቀባይነትን ያገኘው ድምፃዊ፤ የግጥምና ዜማ ደራሲ ብስራት ሱራፊል አበበ ሁለተኛ ስራ የሆነው “ማለፊያ” አልበም ሀምሌ 14 ቀን 2015 ዓ.ም ለአድማጭ እንደሚቀርብ ተገለፀ፡፡ ይህንን የገለፀው በሙዚቃ ኢንዱስትሪው በስፋት የሚንቀሳቀሰውና የብዙ ሙዚቀኞችን ስራ በማስተዋወቅ የሚታወቀው “ኤላ ቲቪ” ከድምፃዊው ብስራት ሱራፌልና ከግጥምና ዜማ ደራሲው ዓማየሁ ደመቀ ጋር በመሆን በትናንትናው ዕለት ረፋድ በሀገር ፍቅር ቴአትር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ነው፡፡ በቀደመው የመጀመሪያ አልበሙና እንደ “ሆንሽብኝ የቤት ስራ” ባሉት ነጠላ ዜማዎቹ እንዲሁም ለተለያዩ አንጋፋና ወጣት ድምፃዊያን በሰራቸው ግጥምና ዜማዎቹ ተቀባይነትና አድናቆትን ያገኘው ብስራት ሱራፌል አልበሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ 4 ዓመታትን እንደወሰደ ገልፆ በአጠቃላይ የአልበሙ ስራ ላይ በርካታ እውቅ ባለሙያዎች መሳተፋቸውም አብራርቷል፡፡ በቅንብሩም አበጋዝ ክብረወርቅ ሺዎታ፤ ታምሩ አማረ፤ ሚኪ ሀይሌ፤ ሱራፌል የሺጥላ፤ ፋኑ ረዳቦና ስማገኘሁ ሳሙኤል፤ የተሳተፉ ሲሆን በግጥም በኩል ዓማየሁ ደመቀ ፍሬዘር አበበ ወርቁ፤ ምልዕቲ ኮሮስ፤ ወንደሰን ይሁብ እና አብዲ ሲሳተፉ ሁሉንም ዜማ ራሱ ብስራት ሱራፌል መስራቱም ተገልፃል፡፡ አርቲስት ብስራት ሱራፌል አዲሱን አልበሙን ካስመረቀ በኋላ በአዲስ አበባ፣ በክልል ከተሞችና በተለያዩ የውጪ ሀገራት ኮንሰርቶችን በመስራት ከአድናቂዎቹ ጋር በመድረክ እንደሚገናኝ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ተብራርቷል፡፡

 በሙዚቃ ሥርጭትና ግብይት የሚታወቀው ሰዋሰው መተግበሪያ፤ የሰዋሰው ፖድካስቶች ኔትዎርክ ሥርጭትን በይፋ አስጀመረ፡፡
ከትላንት በስቲያ ሐሙስ በኃይሌ ግራንድ ሆቴልና ስፓ የሰዋሰው ፖድካስቶች ኔትዎርክ ማስጀመሪያ ሥነሥርዓት የተካሄደ ሲሆን፤ የሥራና ክህሎት ሚኒስትር አቶ ንጉሱ ጥላሁን መድረኩን በይፋ ከፍተውታል፡፡  
ሰዋሰው ፖድካስቶች ኔትዎርክ፤ ተጨማሪ የመዝናኛ የመማማሪያ፤ ሃሳብን የማስተላለፊያና ስሜትን የመግለጫ አማራጭ እንደሚሆንም ተናግሯል፡፡
በእለቱ፣ “የፖድካስት ሚዲያ ዕምቅ አቅምና አስተዋፅኦ” በሚል ርዕስ የፓናል ውይይት ተካሂዷል፡፡
“ሃሳብ ያለው ሃሳቡን በተደራጀ መንገድ፤ ተሰጥኦ ያለው ክህሎቱን በሚስብና አዝናኝ በሆነ አቀራረብ እንዲያስተላልፍ በሚያስችል መንገድ የተመሰረተው ሰዋሰው ፖድካስቶች ኔትዎርክ፤ የሥነልቦና የህግ፤ የሥነፅሁፍ፤ የታሪክ፤ የሙዚቃና ሌሎች ባለሙያዎች የሚሳተፉበት ባለ ብዙ ቀለም የግንኙነት አውታር ነው” ተብሏል፡፡
የተለያዩ የንግድ ተቋማት ከፖድካስቱ ጋር በጋራ እንዲሰሩም ጥሪ ቀርቧል፡፡
ሁሉም ድምፆች በእኩል መጠን ማስደመጥን ዓላማው አድርጎ እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው ሰዋሰው ፖድካስቶች ኔትዎርክ፤ ሰዋሰው መልቲ ሚዲያ የሥነጥበብና እደ ጥበብ ዘርፉን ለማዘመን በእቅድ ከያዛቸው ዘርፎች መካከል አንዱ መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

ድርጅቱ ኮሜዲያን በረከት በቀለን (ፍልፍሉን) የብራንድ አምባሳደር አድርጓል


       መነሻውን አሜሪካ ሀገር ባደረገውና በዘመናዊ ቴክሎጂ የታገዘ አገልግሎት ለማህበረሰቡ ለመስጠት በተቋቋመው ካዛብላንካ ኃ/የተ/የግል ማህበር አማካኝነት የበለፀገው “ካዛሮድ”  የተሰኘ ለመኪኖች ብልሽት መፍትሄ የሚሰጥ አዲስ መተግበሪያ ይፋ ሆነ።
በኢትጵያዊው ዲያስፖራ ሀሳብ አምነጪነት የተቋቋመው ካዛብላንካ፤ ኢትዮጵያዊያን ባለሃብቶችና አሜሪካ የሚገኙ ዲያስፖራዎች ካቋቋሙት “Habesha Spot LLc” ከተሰኘ ተቋም ጋር በመተባበር የበለጸገ መተግበሪያ ሲሆን ይህ ቴክኖሎጂ በተለይም መንገድ ላይ በተሽከርካሪዎች ላይ የሚገጥሙ ችግሮችን እንደሰለጠነው ዓለም በአፋጣኝ መፍትሄ በመስጠት በኩል ኢትዮጵያ ውስጥ በተለይም አዲስ አበባ ላይ ያለውን መጠነ ሰፊ የተሽከርካሪ ብልሽት ችግር እንደሚቀርፍ የድርጅቱ ሃላፊዎች ከትላንት በስቲያ ሰኔ 28 ቀን 2015 በስካይ ላይት ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል። በአራት ቋንቋዎች ማለትም በአማርኛ፣ በእንግሊዝኛ፣ በትግሪኛና በኦሮሚኛ ቋንቋዎች አገልግሎት ይሰጣል የተባለው “ካዛሮድ” መተግበሪያ፣መንገድ ላይ ድንገት ተሽከርካሪ ቢበላሽ፣ ጎማ ቢፈነዳ፣ ባትሪ ወይም ነዳጅ ቢያስፈልግና ማንኛውም ችግር ቢገጥም በካዛሮድ መተግበሪያ ወይም በ8182 የጥሪ ማዕከል በመደወል ብቻ በቀላሉ ችግሩን መፍታት ይቻላል ተብሏል።
ድርጅቱ በአሁኑ ሰዓት ወደ ስራ ለመግባት ከ18 የኢንሹራንስ ኩባንያዎች፣ ከጭነት ተሽከርካሪ ባለንብረቶችና ከባለድርሻ አካላት ጋር ስምምነቶች ላይ የደረሰ መሆኑን የገለጹት ሃላፊዎቹ፤ በቀጣይነትም ከትራፊክ ማኔጅመንትና  ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን ጋር በመተግባበር ያለአግባብ በየመንገዱ እየቆሙ የትራፊክ መጨናነቅ የሚፈጥሩ ተሽከርካሪዎችን በማንሳት መፍትሄ ለመስጠት ዝግጅቱን እያጠናቀቀ  መሆኑም ተብራርቷል። ድርጅቱ፤ ኮሚዴያን በረከት በቀለን (ፍልፍሉን) ለቀጣይ አንድ ዓመት ሥራውን እንዲያስተዋውቅለት የብራንድ አምባሳደር አድርጎ ሾሟል፡፡ “ካዛሮድ” ወደ ስራ መግባቱን ይፋ ለማድረግ የሚመለከታቸው የመንግስት የሥራ ሃላፊዎች፤ ባለድርሻ አካላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ዛሬ ከቀኑ 10፡00 ጀምሮ በስካይ ላይት ሆቴል የማስጀመሪያ መርሃ ግብሩን ያከናውናል። ተቋሙ በቀጣይ በሌሎች ችግር ፈቺ የቴክኖሎጂ ውጤቶች ማህበረሰቡን የማገልገል እቅድ እንዳለውም ሀላፊዎቹ አብራርተዋል፡፡

በኢትዮጽያ ከተለያዩ የሕጻናት ማሳደጊያ ማዕከላት ወጥተው ወደ ሕብረተሰቡ የሚቀላቀሉ ወጣቶች ዘርፈ ብዙ  ተግዳሮቶች እንደሚገጥሟቸው ተገለጸ፡፡ኤስ.ኦ.ኤስ የሕጻናት መንደር፤ በኢትዮጵያ ያሉ የተለያዩ ወጣቶችና ታዳጊዎች ጋር ተያያዥነት ያላቸው የፖሊሲ ክፍተቶችን አስመልክቶ፣ “Policy Gap Assessment and Situational Analysis on Young care Leavers in Ethiopia“ በሚል ርዕስ በባለሙያዎች ያስጠናውን የዳሰሳ ጥናት  ሰኔ 23 ቀን 2015 በሳፋየር አዲስ ሆቴል ይፋ አድርጓል፡፡
ጥናቱ በኤስ.ኦ.ኤስ የሕጻናት መንደር አስተባባሪነት፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ሶሻል ወርክ ትምህርት ቤት መምህራን አማካኝነት የተጠና ሲሆን፤ በአዲስ አበባ የሚገኙ 25 የአማራጭ ክብካቤ ሰጪ ተቋማት፣ አምስት የትኩረት ቡድኖች እንዲሁም ከእነርሱ ጋር የተያያዘ ሥራን የሚሰሩ የመንግሥት የሥራ ሃላፊዎች በጥናቱ መሳተፋቸው ተገልጿል፡፡
በዚህም ከሕጻናት ማሳደጊያ ማዕከላቱ 18 ዓመት ሞልቷቸው ወይንም በተቋማቱ የነበራቸውን ቆይታ አጠናቀው የሚወጡ ወጣቶች ወደ ማህበረሰቡ ሲቀላቀሉ፤ የመኖሪያ ቤት፣ የነዋሪነት መታወቂያ፣ የሥራ ዕድል የማግኘት ችግር እንዲሁም፤ በማህበረሰቡ የመገለልና በቀላሉ የመቀላቀል ችግሮች በከፍተኛ ደረጃ እንደሚያጋጥማቸው ተመላክቷል፡፡በተጨማሪም ወጣቶቹ ከማዕከላቱ ሲወጡና ወደ ማህበረሰቡ መቀላቀል ሲጀምሩ ኹሉም ነገር አዲስ እንደሚሆንባቸው የተገለጸ ሲሆን፤ በዚህም በአጉል ሱሶች የመጠመድ፣ ሴቶች ለሴተኛ አዳሪነት የመጋለጥ እንዲሁም በተለያዩ የወንጀል ተግባራት ላይ የመሳተፍ እድላቸው ሰፊ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ወጣቶቹ ሥራ አግኝተው መስራት ቢጀምሩ እንኳን የገንዘብ አያያዝ ላይ ችግር እንደሚስተዋልባቸው የተነገረ ሲሆን፤ የግል ሥራዎችን ለመስራትም ብድር የማግኘትና ብድሩን ቢያገኙም እንኳን ለብድሩ ማስያዥያ የሚሆን ዋስትና የማግኘት ተግዳሮት እንደሚያጋጥማቸውም በዳሰሳ ጥናቱ ተመላክቷል፡፡በተለይም ከማዕከላቱ በሚወጡ አካል ጉዳተኛ ወጣቶች ላይ ችግሩ ከፍተኛ መሆኑ የተነገረ ሲሆን፤ በትምህርት ቤቶች ደረጃም ከሕጻናት ማሳደጊያ ማዕከላት ለሚወጡ ወጣቶች ያለው አመለካከት ዝቅተኛ ነው ተብሏል።
ይህን ችግር ለመቅረፍ ኹሉም ዜጋ ሃላፊነት እንዳለበትና በተለይም መንግሥታዊ ተቋማት ትኩረት በመስጠት ችግሩ በፖሊሲ መፍትሄ እንዲያገኝ መስራት እንደሚጠበቅባቸው ተነግሯል።
በዚህም መሰረት፤ ከሕጻናት ማሳደጊያ ማዕከላት የሚወጡ ወጣቶችን የሚያግዙ ደጋፊ ፖሊሲዎች/ ህግጋት እንዲወጡና እንዲተገበሩ የሚመለከታቸውን አካላት ግፊት ማድረግ ያስፈልጋል የተባለ ሲሆን፤ ለወጣቶቹ ፍላጎቶችና መብቶች ተገቢውን ምላሽ እንዲሰጡ ማስቻል ይገባልም ተብሏል፡፡ በተጨማሪም በመሻሻል ላይ በሚገኘው የብሔራዊ የወጣቶች ፖሊሲ ላይ ከሕጻናት ማሳደጊያ ማዕከላት የሚወጡ ወጣቶች ጉዳይ ሊካተት እንደሚገባው ተነግሯል፡፡ እንዲሁም ወጣቶቹ መብቶቻቸውን የሚጠይቁ እንዲሁም በማንኛውም አገራዊ ጉዳይ ላይ ንቁ ተሳታፊ እንዲሆኑ ማስቻል እንደሚገባም በዳሰሳ ጥናቱ ላይ ተመላክቷል፡፡ ለወጣቶቹ ሥራ በመፍጠርና አስፈላጊ የህይወት ክህሎት ስልጠናዎችን ለመስጠት የሚመለከታቸው የመንግሥት አካላትና ተቋማቶቹ በትብብር ሊሰሩ እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡በመድረኩ ጉዳዩ የሚመለከታቸው መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት የተገኙ ሲሆን፤ በጥናቱ ላይም ሰፊ ውይይት ተካሂዷል፡፡ የመድረኩ ተሳታፊዎች የተጠናው ጥናት ለመንግሥት ጥሩ ግብዓት እንደሚሆን በመግለጽ፤ ከወጣቶቹ ነባራዊ ሁኔታ በመነሳት የፖሊሲ ክፍተቶቹን ለመድፈን በርብርብ መስራት እንደሚያስፈልግ ጠቁመዋል፡፡

 “የጓሮ ማህረሰብ ንቅናቄ” (Home Gardening commiunity) ከውብና ማራኪ ነርሰሪ (አትክልት ማዘጋጃና መሸጫ) ጋር በመተግበር ከ6-17 ዓመት እድሜ ላላቸው ልጆች ስልጣና ሊሰጥ ነው። ስልጠናው ልጆች የህልውናቸው መሰረት የሆነውን ተፈጥሮን፣ ግብርናንና አካባቢያቸውን በተገቢው መንገድ እንዲያውቁና እንዲገነዘቡ ብሎም ተፈጥሮን የመንከባከብ ዝንባሌና ፍላጎት እንዲያድርባቸው የሚያግዝ ስለመሆኑ የጓሮ ማህበረሰብ ንቅናቄ ማህበራዊ ድረገጽ መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ስለሺ ባዬህ ተናግረዋል። የስልጠናው ማስጀመሪያ መርሃ ግብር ዛሬ ሀምሌ 1 ቀን 2015 ዓ.ም ለቡ መብራት አጠገብ በሚገኘው ነርሰሪ (የአትክልት ማዘጋጃና መሸጫ) ሥፍራ ላይ የሚከናወን ሲሆን፣ በዕለቱም በዘርፉ ከ30 ዓመት በላይ ልምድ ያላቸው ተረፈ በልሁ (ዶ/ር) ያላቸውን ልምድ እንደሚያካፍና፣ አትክልት ነርሰሪውም እንደሚጎበኝ ተገልጿል። የጓሮ ማህበረሰብ ንቅናቄ ወላጆች ነገ ሀገር ተረካቢ የሆኑና ከ6-17 ዓመት እድሜ ያላቸውን ልጆቻቸውን በዚህ ሥልጣና በማሳተፍ ከወዲሁ ልጆቻቸው ከተፈጥሮ፣ ከግብርናና ከአካባቢያቸው ጋር ያላቸውን ቁርኝት እንዲያጠናክሩና ለተፈጥሮ ፍቅር ያላቸው ተተኪ ዜጎችን በማፍራቱ በኩል የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጥሪ ቀርቧል። የጓሮ ማህበረሰብ ንቅናቄ ማህበራዊ ድረገፅ የኮቪድ 19 ወረርሽኝ መከሰትን ተከትሎ የተመሰረተ ሲሆን ዓላማውም በወረርሽኙ ወቅት ሊከሰት የሚችለውን ማህበራዊ ቀውስ ለማቃለልና ማህበረሰቡን ለማነቃቃት ታስቦ በግለሰቦች የተቋቋመ ንቅናቄ መሆኑ የሚታወስ ሲሆን፣ ባለፉት 3 ዓመታት በማህራዊ ትስስር ገጽ፣ በህትመት ሚዲያና በሰርቶ ማሳያዎች ስለተፈትሮ፣ ስለግብርና፣ ስለአካባቢ ጥበቃና ስለከተማ ግብርና ፋይዳ የመማማሪያ መድረኮችን በመፍጠር ከፍተኛ አስዋጽኦ ያደረገና እያደረገ እንደሚገኝም አቶ ስለሺ ባዬህ ለአዲስ አድማስ ጨምረው ገልጸዋል።




 በጥንት ዘመን እድሜውን በሙሉ በመድከምና በመልፋት ሃብት ያፈራ ባለፀጋ ሁለት ልጆች ወልዶ በአንድ አገር ይኖር ነበር። ልጆቹም አንዱ ብርቱና ጎበዝ ሲሆን፣ ሌላው ግን ሰነፍና ደካማ ነበር።
ባለፀጋው ወደ ሽምግልና ዕድሜው ሲደርስ ልጆቹን አስጠራና መመካከር ያዙ።
“ልጆቼ እንደምታዩኝ እርጅና እየተጫጫነኝ ነው። እግዚአብሔር ይመስገንና ባገሪቱ ካሉት ከበርቴዎች አንዱ ብሆንም የኔ ሃብት የኔ ሆኖ የሚቆየው ልሰራበት የሚያስችል ዓቅምና ስልጣን ኖሮኝ ስገኝ ብቻ ነው። ያለበለዚያ ግን ሃብቴም ይባክናል፣ እናንተ ልጆቼም በማመስገን ፋንታ “ኤጭ ወዲያ” ብላችሁ ሞቴን ትመኙልኛላችሁ ሲል፡-
ልጆቹ አቋርጠውት በአንድነት “አባባ ምነው ያለወትሮህ እንዲህ ያለ አስፈሪ ነገር ትናገራለህ?” ብለው ጠየቁት።
“አደራ ልጥልባችሁ ነው” አለና ቀጠለ አባት። “እስከዛሬ ካፈራሁት ሃብት ግማሹን አኑሬ ግማሹን ለሁለታችሁ ላካፍላችሁ ወስኛለሁ”
ልጆቹም በየተራ “አባታችን ስለአሰብክልን እናመሰግንሃለን ከቃልህም አንወጣም” አሉና ጉልበቱን ሳሙ።
አባትየውም የሃብቱን ገሚስ ለሁለት ከፍሎ እኩል እንዲካፈሉ የፈረመበትን ሰነድ ሰጣቸውና፣ መርቆ ወደፈለጉበት አገር ሄዶ ሰርቶ ከመኖር ነፃነት ጋር አሰናበታቸው።
ከዚያን ቀን አንስቶ ሁለቱም ወደተለያየ ቦታ ተሰማርተው፣ ትዳር መሥርተው መኖር ጀመሩ። ልጆች ወልደው በተናጠል አባታቸውን እየጠየቁ እነሱ ግን ሳይጠያየቁ ዓመታት አለፉ።
ሁለቱ ልጆች በአንድ ሳምንት ውስጥ ተከታትለው ሞቱና አንዱን ቀን መርዶአቸው ለሽማግሌ አባት መጣለት። ሀዘኑን ባገር ወግ ተቀምጦ ሰነበተና መርዶ አምጪዎቹን ስለልጆቹ ያሟሟት ሁኔታ ጠየቀ። ብርቱው ልጁ በእህል ጥጋብና በቁንጣን፣ ደካማው ደግሞ በስንፍናና በችጋር መሞታቸው ተነገረው።
ሽማግሌውም ይኸንን የልጆቹን ባህርይ ቀድሞ ለምን እንዳላሰበበት ሲቆጭ ሰነበተና፤ “ሰነፉ ልጄ የሞተበት ብርቱው ልጄ የሞተበት ለሰነፉ ልጄ ´መድሐኒት´ ሊሆናቸው ሲገባ ወየው ልጆቼ ያለመጠያየቃችሁና ያለመተሳሰባችሁ ጎዳችሁ” በማለት አንብቦ አዘነ።
ቀጥሎም ስለ ልጅ ልጆቹ ጠባይና አመል ጠየቀ። የሰነፉ ልጅ በተቃራኒው ብርቱ መሆኑንና የብርቱው ልጅ እንዲሁ ሰነፍ መሆናቸው ተነገረው።
የእግዚአብሔር ተዓምር አያቅም እያለ ሲገረም ከቆየ በኋላ፣ ከአጠገቡ ሳይርቁ እንዲኖሩ አዝዞ እየሰራችሁ እደጉ በማለት የተራረፈውን ንብረት አካፈላቸው።
የልጅ ልጆቹም በየፊናቸው የየአባታቸው ሞት ጥልቅ ሀዘን እየተሰማቸው፤ አባቱን በጥጋብ የሞተበት የአባቱ አይነት ሞት እንዳይደርስበት እስኪጠግብ ከመብላት እራሱን አግዶ፤ በችጋር መኖር ስለጀመረ እየከሳና እየጠወለገ መስራትም እያቃተው ይሄድ ጀመር።
አባቱ በችጋር የሞተበት ደግሞ የአባቱ አይነት አሟሟት እንዳይገጥመው ያለመጠን እየበላ ያለቅጥ በመወፈሩ መስራት አቃተውና እቤት ዋለ።
አያታቸውም እንደዚህ የሆነበት ምክንያት ቢጠይቅ ሁለቱም አባታቸው የሞቱበት ምክንያት ለመከላከል በወሰዱት እርምጃ ነበር።
አያታቸው መጀመሪያ ለሰነፉ “የብርቱውን አባትህን ሞት ፈርተህ አካልህን ምግብ ብትከለክለው የሰነፉ አጎትህ ሞት ያጋጥምሃል፡፡” አለው። ቀጠለና ለብርቱው “የሰነፉን አባትህን ሞት ፈርተህ አካልህን ያለቅጥ ብትመግበው የብርቱው አጎትህ ሞት ያጋጥምሃል” ካለ በኋላ ለሁለቱም፤”ልጆቼ ጨርሰው ሲራቡም ጨርሰው ሲጠግቡም ሞት ይከተላል። ከአባታችሁ ሞት ተማራችሁ? የሚባለው በልክ ሰርታችሁ በልክ መመገብ ስትችሉ ብቻ ነው። መፍራት ያለባችሁ የራሳችሁን ተግባር እንጂ የአባቶቻችሁን ሞት አይደለም። መፍራት ያለባችሁ የአባቶቻችሁን ያለመጠያየቅና ያለመከባበር ነው። ማለት ያለባችሁ እኔ የአባቴንም የአጎቴንም ጥፋት አልደግመውም ነው” አላቸው ይባላል።
***
የኢትዮጵያ ህዝብ በቋንቋው ቢለያይም በመከራው ግን በደም፣ በባህል፣ በስነ-ልቦና፣ በታሪክ… ወዘተ አንዱ የአንዱ የሥጋ ዘመድ ነው። ወይ አጎት፣ ወይ አክስት፣ ወይ ዋርሳ፣ ወይ አያት፣ ወይ የአያት ልጅ ነው። ሲቀናቀን ቢኖር እውነታው ከዚህ አይዘልም። ንግግሩ ከሚዛን እንዳይዘናበልበት አባቴ ምን ደረሰበት? ብቻ ሳይሆን አጎቴስ? የማለት ባህርይ ከትውልድ ትውልድ እየተላለፈ እዚህ አድርሶታል።
“ማሩን ለራስ መርዙን ለጎረቤት” እንዳንባል የራስን ብቻ ሳይሆን የአጎትንም ጨምሮ ማየት አስተዋይነት ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ የአጎቱንና የአባቱን መከራ አዛምዶ እያጤነ፣ ከተሞክሮ እየተማረ፣ ዛሬም ሳይነጣጠል እጅ ለእጅ ተያይዞ ለመራመድ እየጣረ ነው።
ፓርላማው የዚህ ጥረቱ ዓቢይ ምሳሌ ነው። ፓርላማው ከነጉድለቱ የአገሪቱ ከፍተኛ ውሳኔ ሰጪ መሆኑ ታውጇል።
“የምትጠጣበትን ጉድጓድ ደንጊያ አትጣልበት” እንዲል መጽሐፉ፤ በዚህ በተከበረ የሕዝብ ሸንጎ ፊት የሚደረግ ስላቅ እልህና ዘለፋ የሀገሪቱን ግርማ ሞገስ ዝቅ አድርጎ የሚያስንቀን እንዳይሆን መጠንቀቅ ይበጃል።
የምክር ቤቱን አባላት “የተከበሩ አቶ/ወ/ሮ እገሊት” ብለን የምንጠራቸው የግል ፍቅራችን አነሳስቶን ሳይሆን ለወከሉት ህዝብ ያለንን አክብሮት ለመግለጥ ጭምር ነው። ፓርላማውን የሚያከብር አባላቱን ያከብራል። አባላቱን ማክበር ማለት የመረጣቸውን ህዝብ ማክበር ማለት ነው። አባላቱን ስናሽሟጥጥና በእነሱ ላይ ስንሳሳቅ የላካቸውንና የወከላቸውን ህዝብ ምን እያልነው እንደሆን ከወዲሁ ማጤን ይገባል።
አባቴ ሲቆጣ አጎቴን እያሰበ ካልሆነ፣ በዓይነቱ የተጠየቀው በዚያው በዓይነቱ ካልተመለሰ ወደ ስድብና ናጫ ያመራል። አበው ሲሸመግሉ “እምባጓሮና የውሃ ሙላት ከጨመሩባቸው ይበረታሉ” የሚሉትም ለዚህ ነው። ያበለዚያ ግን “ዓሳማ ንጹህ መሆኑን ለማሳየት እግሩን ያነሳል” መባል ይከተላል።
“ጀግና ማለት በመጀመሪያም በመጨረሻም የገዛ ባህርይውን ያሸነፈ ነው” ማለት ይህን ይመስላል። ቁጣ፣ እልህ፣ መገሰልና ሌሎችን መናቅ፣ የጎበዝ ምልክት አይደለም። ቧልትና ተሳልቆ በቤተ-መቅደስ ውስጥ ሲካሄድ “ቅዳሴው ሲያልቅበት ቀረርቶ ሞላበት”ን ያስተርታል። “የጀግና ሰው ጌጡ ትህትናው ነው” እንዲል መጽሐፍ  ከዘለፋው ትህትናው ሊቀድም ይገባል። ምክር ቤት የገባው አባል የአባቴም የአጎቴም ወኪል ነው እናም ወኪሌና ወኪላቸው ሲነጋገሩ “ዳኛ ሆነህ ስትሰየም እንደ ጠበቆች አትሁን” የሚለውን ብሒል ሳይዘነጉ መሆን አለበት።
የሚያስቆጣውና ዘለፋ ውስጥ የሚያስገባው የሌሎች ሀሳብ መስጠት ከሆነ፣ ሌሎችን አላዳምጥም ማለት የት እንዳደረሰን የእራሳችንን ታሪክ ማስታወስ ይበቃል።
ቡድን እንደ ደንጊያ ክምር ነው። በተለይም ያ! ቡድን በጉልበተኛና በማን አህሎኝ የሚመራ ከሆነ የቡድኑ አውራ ሲመዘዝ ክምሩ እንደሚናድ መጠራጠር አይገባውም። ስልጣንና ክብር በራሳቸው እግር ሲቆሙ ያዛልቃሉ። ምርኩዝ ግን ምንጊዜም ምርኩዝ ነው።
ጎበዝ ያነሰበትን ሰፈር እያሸሟቀቁ የደካሞች ዓለቃ፣ የሰነፎች አውራ ላለመሆን ልብ ያለው ልብ ይበል። ለፍቶና ደክሞ ያለፈለት ሰው ድኅነት፤ ሳይለፋ የበለጸገውን ሰው ትክክለኛነት አያሳይም። “የተቆለፈ ደጃፍ በቶሎ አይከፈትም” እንዲሉ፣ የሚጠራኝ ይበዛል ብሎ ለገመተ የሚወደድበትን ብልሃት ቢያዘጋጅ ይበጀዋል።
“የሰው ልጅ ጊዜውን እቃም ቦታውን ሳያገኝ አቀርምና ሁሉንም አትናቅ” እንዳለው መጽሐፈ ምሳሌ… አነሰ በዛ፣ ጠቆረ ቀላ፣ ሳንል ትህትናንና አክብሮትን በማስቀደም ምሳሌ መሆን ካሻን “ፍም እፍፍ ቢሉትም ይነዳል፣ እንትፍ ቢሉትም ይጠፋል” ማለትን እንልመድ!! እንከተል!!



*አክሲዮኑ ከ10 ሺ ብር እስከ 50 ሚ. ብር ለሽያጭ ቀርቧል

*ሁሉም ኢትዮጵያዊ አክሲዮኑን እንዲገዛ ጥሪ ቀርቧል


በአማራ ክልል ደቡብ ወሎ መካነ ሠላም፣ የሲሚንቶና ዘይት እንዲሁም ብረትና ቢራ ፋብሪካዎችን  ለማስገንባት የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን ማጠናቀቁን የጠቆመው ኖርዝ ኢስት ትሬዲንግ አክሲዮን ማህበር፤የአክሲዮን ሽያጭ በይፋ መጀመሩን አስታወቀ፡፡

አክሲዮኑን የሃገር ውስጥ ባለሃብቶች፣ ዳያስፖራዎችና በዘርፉ ለመሳተፍ ፍላጎት ያላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች መግዛት እንደሚችሉ የገለጸው ድርጅቱ፤ አክሲዮኑ ከ10ሺ ብር እስከ 50 ሚ. ብር ለሽያጭ መቅረቡን ጠቁሟል፡፡

የአክሲዮን ሽያጩ በይፋ መጀመሩን አስመልክቶ የኖርዝ ኢስት ትሬዲንግ አክሲዮን ማህበር አደራጅ ቦርድ፣ በዛሬው ዕለት ጠዋት ረፋድ ላይ አራት ኪሎ፣ አሚኮ ያለበት ህንጻ 2ኛ ፎቅ ላይ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ እንደተጠቆመው፤ ሃገር ወዳድ በሆኑ ጥቂት ባለ ራዕይ ምሁራንና ባለሃብቶች ሃሳብ አመንጪነት የተጠነሰሰው ኖርዝ ኢስት ትሬዲንግ አክሲዮን ማህበር፣ ወደ ሥራው ለመግባት በዙሪያው አቅም ዕውቀትና ክህሎት ያላቸውን ቀናኢ የሆኑ ባለሃብቶች በማሰባሰብ በርካታ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል፡፡

እስካሁን ድርጅቱ ለሥራው አስፈላጊ የሆኑ ልዩ ልዩ አደረጃጀቶችን በመፍጠር፣ ጽ/ቤት በማቋቋም፣ የማዕድን ምርመራ ፈቃድ በመውሰድ፣ በአጋርነት አብረው ሊሰሩ የሚችሉ የውጭ ባለሃብቶች በማፈላለግ፣ የህዝብ ግንኙነት ሥራዎችን በመሥራት አመርቂ ውጤት ማስመዝገቡን የጠቆሙት የአደራጅ ቦርድ አባላት፤ አሁን ሃብት ወደ ማሰባሰብ ተግባር ለመሸጋገር የአክስዮን ሽያጩ በይፋ ተጀምሯል ብለዋል፡፡

የክልሉ መንግሥት አብሮን ለመሥራት ከፍተኛ ፍላጎት አሳይቷል ያሉት የአደራጅ ቦርድ አባላቱ፤ ለግንባታ የሚሆን ቦታ መረከባቸውንም ጠቁመዋል፡፡

ኢንቨስትመንቱን በደቡብ ወሎ መካነ ሠላም ለማድረግ ለምን እንደመረጡ ከጋዜጠኞች የተጠየቁት የቦርዱ አመራሮች፤ “አካባቢውን የመረጥነው የሲሚንቶ ምርት ግብአቶች በብዛት የሚገኝበትና  ለጅቡቲ ወደብ ቅርብ በመሆኑ ነው፡፡“ ብለዋል፡፡   

የአደራጅ ቦርድ አባላቱ አክለውም፤አካባቢው ለሲሚንቶ ምርት ከሚያስፈልጉ ግብአቶች  በተጨማሪ የተለያዩ  የከበሩ ማዕድናት መገኛ መሆኑንም ገልጸዋል፡፡

በኖርዝ ኢስት የሚከናወነው ከፍተኛ ኢንቨስትመንት በአሁኑ ወቅት በተለይ አገሪቱ የገጠማትን የሲሚንቶና የዘይት ምርት እጥረት ከማቃለሉም ባሻገር በ10ሺ ለሚቆጠሩ ዜጎች የሥራ ዕድል እንደሚፈጥር የጠቆሙት የአደራጅ ቦርድ አባላቱ፤  ሁሉም ኢትዮጵያዊ ድርጅቱን በመቀላቀል አብሮአቸው  እንዲሰራ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

“ሃብት ያለው አክሲዮን በመግዛት፣ ዕውቀት ያለው በዕውቀቱ፣ ጊዜ ያለው በጊዜው ሁሉም አብሮን እንዲሰራ ነው የምንፈልገው“ ብለዋል፤በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ባስተላለፉት መልዕክት፡፡

ከአክሲዮን ሽያጩ 11.2 ቢሊዮን ብር ማሰባሰብ እንደሚጠበቅባቸው የጠቆሙት  የአደራጅ ቦርድ አባላቱ፤ሽያጩ  በማንኛውም ባንክ እንደሚከናወንም አስታውቀዋል፡፡ 

ኖርዝ ኢስት ትሬዲንግ አክሲዮን ማህበር፣ መጋቢት 25 ቀን 2014 ዓ.ም፣ የተቋቋመ ድርጅት ነው፡፡

Page 12 of 665