Administrator

Administrator

የሠራዊት አባላቱ ጠ/ሚኒስትሩንና ህዝቡን ይቅርታ ጠይቀዋ

ባለፈው ረቡዕ መስከረም 30 ቀን 2011 ዓ.ም ተሲያት ላይ፣ 240 የመከላከያ ሰራዊት አባላት፣ ከእነ ሙሉ ትጥቃቸው ወደ ብሔራዊ ቤተ-መንግስት ያመሩት ለግዳጅ  አልነበረም። ይልቁንም ከጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ጋር ለመወያየት ፈልገው ነው፡፡ የሰራዊት አባላቱ ያልተለመደ አመጣጥ እንግዳ የሆነባቸው የቤተ መንግስት ጸጥታና ደህንነት ሃላፊዎች፤ ከሁሉ አስቀድመው አባላቱን ትጥቅ እንዳስፈቷቸው  ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ከዚያ በኋላ ነው ቤተ መንግስት እንዲገቡ የተፈቀደላቸው ተብሏል፡፡
ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ፣ የዚያኑ ዕለት ምሽት ለኢቴቪ በሰጡት መግለጫ፤ ነገሩን ቀላል አድርገው ነው የገለጹት፡፡ በወታደሮቹ ቤተ መንግስት መከሰት የደነገጡ ወይም የተበሳጩ አይመስሉም፡፡ እንደውም ከሰራዊቱ አባላት ወደ ቤተ መንግስት መግባት ጋር ተያይዞ፣ በፌስቡክ ላይ በተሰራጩ የ”መፈንቅለ መንግስት ሙከራ” እየተደረገ ነው ዓይነት አሸባሪ የፈጠራ ወሬዎች ሳይደነግጡ አልቀሩም፡፡ ለዚያም ሳይሆን አይቀርም ራሳቸው ለቲቪ መግለጫውን የሰጡት። “የውሸት ዘመቻ ተቀብለን ካስተናገድን ያው መበላላት ነው” ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ”በሃይማኖት፣ በዘር፣ በሥልጣን---ክፉ ሰዎች እንዲህ እየፈጠሩ ነው የሚያሰራጩት--” በማለት ህብረተሰቡ፣ ከፌስቡክ ዘመቻ ራሱን እንዲያቅብ መክረዋል፡፡    
ጠ/ሚኒስትሩ ነገሩን ቀለል ያድርጉት እንጂ ፖለቲከኞችና ምሁራን ግን የወታደሮቹን ድርጊት እንደ አደገኛ አዝማሚያ በመቁጠር መንግስት ዳግም እንዳይከሰት ወሳኝ እርምጃ መውሰድ አለበት ይላሉ፡፡  
“የሠራዊት አባላቱ የትኛውም ዜጋ ደፍሮ የማያደርገውን አማራጭ በመውሰድ፣ ትጥቅ ይዘው በአስገዳጅ ሁኔታ ቤተ መንግስት መግባታቸው አደገኛ መልዕክት ያለው ነው” ያሉት የዩኒቨርሲተ መምህሩ አቶ ስዩም ተሾመ፤ ”የሠራዊቱ አባላት ይህን ድርጊት ለመፈፀም የደፈሩት ስለታጠቁ ብቻ ነው፤ ይሄ ለሌላውም የሰራዊት አባላት አርአያነቱ በጎ አይደለም” በማለት ያስጠነቅቃሉ፡፡  
ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል የየራሱ ጥያቄ አለው፣ ነገር ግን በእንዲህ መልኩ ማቅረብ የሚችልበት ድፍረትም የህግ አግባብም የለም ያሉት መምህር ስዩም፤ያለ ብዙ ችግር ሁኔታው መጠናቀቁ መልካም ነው፤ ድርጊቱ ዳግም እንዳይሞከር ግን የማስተካከያ እርምጃዎች መውሰድ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
ድርጊቱ በድንገት የተካሄደ ነው ብለው እንደማያምኑ የጠቆሙት ምሁሩ፤ “በሚገባ ተመክሮበትና ታቅዶበት የተደረገ መሆኑ፣ ድርጊቱን አደገኛ አዝማሚያ ያለው ያደርገዋል” ሲሉ ግምታቸውን ሰጥተዋል፡፡ “ጉዳዩን በየደረጃው ያሉ የጦር አዛዦች ያውቃሉ ብዬ እገምታለሁ፤ ማወቅም አለባቸው፤ ለምን የሰራዊቱ አባላት ከቡራዩ ተነስተው 4 ኪሎ እስኪደርሱ በዝምታ ተመለከቱ?” ሲሉ ይጠይቃሉ፤ አቶ ስዩም፡፡  
ምሁሩ እንዲህ ይበሉ እንጂ የሰራዊቱ አባላት በእርግጥም ከቡራዩ ወደ 4 ኪሎ ቤተ መንግስት በቀጥታ መምጣታቸውን  ማረጋገጥ  አልተቻለም።  
በዚህ ጉዳይ ላይ ጥልቅ ምርመራና ፍተሻ ተካሂዶ የማስተካከያ እርምጃ መወሰድ እንዳለበት በአፅንኦት የተናገሩት አቶ ስዩም፤ ብሶታቸውን ለማሰማት በዚህ መንገድ ወደ ቤተ መንግስት ያመሩትን የሰራዊት አባላት በህግ ተጠያቂ ለማድረግ መሞከር ግን ተገቢነት የለውም የሚል አቋም ያንጸባርቃሉ;፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ፤ ብሶታቸውን ሊተነፍሱ ወደ ቤተ መንግስት ያመሩትን የሰራዊት አባላት በተመለከተ በኢቴቪ ብቅ ብለው የተናገሩትን የሰማ ሰው ሁሉ፣ የቱንም ያህል ህገ ወጥ ድርጊት ፈጽመው ቢሆን እንኳን ከፑሽ አፕ የዘለለ፣ ጨከን ያለ እርምጃ ይወሰድባቸው የሚል ሃሳብ ላይሰነዝር ይችላል፡፡ በእርግጥ ትንሽ ተሃድሶ ቢጤ ያስፈልጋቸው ይሆናል፡፡ በድጋሚ ከጠ/ሚኒስትሩ ጋር ለመወያየት ወደ ቤተ መንግስት ጎራ እንዳይሉ።   
የፖለቲካ ተንታኙ ዶ/ር መንግስቱ አሰፋ በበኩላቸው፤ ውትድርና ከሌላው ሙያ በተለየ መልኩ ጥብቅ የስራ፣ የኑሮና የተልዕኮ ዲሲፕሊን ያለው ነው ይላሉ፡፡ “ወታደር ጥያቄ ሲኖረው በየደረጃው ላሉ አመራሮች  ማቅረብ ነው የሚጠበቅበት፤ ድርጊቱ ጥሩ አዝማሚያን አያሳይም” ብለዋል፡፡
“መንግስት በወታደር ዘንድ የሚከበር እንጂ በቀላሉ የሚደፈር መሆን የለበትም” ያሉት አንጋፋው ፖለቲከኛ አቶ ያሬድ ጥበቡ በበኩላቸው፤ የሰራዊት አባላቱ ድርጊት የሚያመላክተው በሰራዊቱ ለቀናት ወይም ለሳምንታት የተካሄደ ምክክር መኖሩን ነው ይላሉ፡፡  
ውይይቱ የተካሄደውም በወታደሮቹ አስገዳጅነት ነው ብለው እንደሚያምኑ የተናገሩት አቶ ያሬድ፤ ወታደሮች ጥያቄ ሲኖራቸው መስመራቸውን ይዘው ባሉበት ይጠይቃሉ እንጂ በምንም አይነት ሁኔታ ወኪል መርጠው፣ ቤተ መንግስት ገብተው፣ ጥያቄ ማቅረብ ሊፈቀድላቸው አይገባም ነበር ብለዋል፡፡
“ከአሁን በኋላ በፈለጋቸው ሰአት እየመጡ ተመሳሳይ ትዕይንት እንደማያደርጉ ምን መተማመኛ አለ?” ሲሉ የሚጠይቁት አቶ ያሬድ፤ “ጠ/ሚኒስትሩና አመራሮቻቸው ሁኔታዎች እንዴት እዚህ ደረጃ እንደደረሱና መፍትሄ መሻት እንዴት እንዳልቻሉ፣ ራሳቸውን መፈተሽ አለባቸው ብለዋል፡፡
የወታደሮቹ ድርጊት በፑሽ አፕ የፎቶ ምስሎች የሚደበቅ ተራ ነገር ሳይሆን ኢትዮጵያ በየቀኑ እየተላመደች የመጣችው ስርአት አልበኝነት አንድ አካል ነው የሚል እምነት እንዳላቸው የገለፁት አቶ ያሬድ፤ የዶ/ር ዐቢይ አህመድ መንግስት፣ ሁለንተናዊ ጥንቃቄ ማድረግ አለበት ብለዋል፡፡
በእርግጥም ብሶታቸውን ለመናገር ቤተ መንግስት የገቡት የሰራዊቱ አባላት፤ ከጠ/ሚኒስትር ዐቢይ ጋር ውይይታቸውን ሲጨርሱ ፑሽ አፕ እንዲሰሩ ተደርገዋል፤ ከዶ/ር ዐቢይ ጋር። ጠ/ሚኒስትሩ የዩኒቨርሲቲ ምሁራንን ባወያዩበት ወቅትም፣ ከጥቂት ወጣት ምሁራን ጋር ፑሽ አፕ መሥራታቸው አይዘነጋም፡፡ በመጨረሻም የሠራዊቱ አባላት፣ ከዶ/ር ዐቢይ ጋር ፎቶ ተነስተው ነው የተለያዩት፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ፤ የሰራዊት አባላቱ ለፈጸሙት ድርጊት፣ በትላንትናው ዕለት፣ ህዝቡንና ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድን ይቅርታ መጠየቃቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡  




 በክብር እንግድነት በተገኙት በምክትል ጠ/ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን መስከረም 30 ቀን 2011 በሚሊኒየም አዳራሽ በድምቀት የተከፈተው 9ኛው አዲስ ቢውልድ ዓለም አቀፍ የኮንስትራክሽን ግብአቶችና ቴክኖሎጂ ኤግዚቢሽን ዛሬ ይዘጋል፡፡
በየትኛውም የአገር ዕድገት ኢኮኖሚ ላይ የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ የሚያበረክተው አስተዋፅኦ በጣም ከፍተኛ ነው ያሉት ም/ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ሀገራችንን ለማዘመን ቁልፍ ከሆኑ ዘርፎች ከፍተኛ ካፒታል የሚጠይቅ፣ ከፍተኛ የሥራ ዕድል የሚፈጠርበትና ለሌሎች የልማት ፕሮግራሞች ስኬት መሰረት የሚሆነው ይኼው ዘርፍ ነው ሲሉ ገልፀዋል፡፡ ዘርፉ፤ በርካታ የሆኑ ገንቢዎች፣ አልሚዎች፣ የግንባታ ግብአት አቅራቢዎች፣ የሥራ ተቋራጮችና ሌሎችም የሚሳተፉበት ከፍተኛ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ማዕከል እንደሆነ የጠቀሱት አቶ ደመቀ፤ ዘርፉን ለማዘመን በአገራዊ አቅም ላይ የተመሰረተ እንዲሆን ማድረግ እጅግ በጣም ወሳኝ ነው ብለዋል፡፡
ይህ ኤግዚቢሽን ለመንግሥት ከፍተኛ ተስፋ የሚያጭርና ተገቢ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው፣ በኮንስትራክሽን ግብአቶች አቅራቢዎችና አገልግሎት ሰጪዎች ላይ ያተኮረ መሆኑ ነው ያሉት ም/ጠ ሚኒስትሩ፣ የልምድ ልውውጥ መድረኮችን በማመቻቸት፣ በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ፣ የአገር ውስጥ የኮንስትራክሽን ግብአቶች፣ አምራቾችና የአገልግሎት ሰጪዎችን የበለጠ እንዲጠናከሩ ማድረግ ያስፈልጋል ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡
የቴክኖሎጂ ሽግግር የተሟላና ሙሉ የሚሆነው፣ ፋና ወጊዎችን በማበረታታት፣ ደረጃ በደረጃ በዓለም ላይ ተወዳዳሪ ማድረግ ሲቻል ነው፡፡ የአገር ውስጥ ግብአት አምራቾችና አቅራቢዎችን በጠንካራ የገበያ ትስስር፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር፣ በኢንጂነሪንግ ፋብሪኬሽን አቅምን በመገንባት፣ ከልዩ ልዩ ከፍተኛ የትምህርት፣ የቴክኒክና የሙያ፣ የምርምርና የቴክኖሎጂ ሽግግር ተቋማት ጋር በማገናኘት መስራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
መንግሥት የዜጎችን ፍላጎት በማስቀደም፣ ለወጣቱና ለመጪው ትውልድ የምትመች ኢትዮጵያን ገንብቶ ለማስረከብ፣ የተለያዩ ስትራቴጂዎችን ቀርፆ ተግባራዊ በማድረግ ላይ ይገኛል ያሉት የኮንስትራክሽን ሚኒስትር ኢንጂነር አይሻ መሐመድ፤ የኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ኢንዱስትሪውን ተወዳዳሪና ትርፋማ በማድረግ ሂደት ውስጥ የተደራጁ የሙያ ማኅበራትን በማበረታታት፣ የሙያ ሥነ ምግባርን በማስረፅ፣ መልካም ተሞክሮዎችን በማስፋት፣ በቴክኖሎጂ ሽግግር ለማሳለጥ፣ የግሉን ዘርፍ ጤናማ ፉክክር ለማዳበር ጥረት እያደረገ ነው ሲሉ ገልፀዋል፡፡
ከ80 በላይ በኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪዎች፣ የኮንስትራክሽን ግብአቶችና ቴክኖሎጂዎች አቅርቦት ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሱ አምራቾች አቅራቢዎችና አልሚዎች የሚገኙበት ይህ ኤግዚቢሽን፤ በአገራችን የኮንስትራክሽን ኢንዱስትሪ እንደ ማነቆ የተቀመጠውን የአገር ውስጥ የኮንስትራክሽን ግብአቶች ችግር፣ ወጪና ጊዜ ቆጣቢ የኮንስትራክሽን እጥረት ለመቅረፍና የተሻለ ኢንዱስትሪ ለመፍጠር፣ ብዙ የልምድ ልውውጥና የቴክኖሎጂ ሽግግር የገበያ ትስስር የሚደረግበት ነው ብለዋል- ሚኒስትሯ ኢንጂነር አይሻ መሐመድ፡፡
ከ9ኛው የኮንስትራክሽን ግብአቶችና ቴክኖሎጂ ኤግዚቢሽን በተጨማሪ፣ 6ኛው አግሮፉድና ፓኬጂንግ እንዲሁም  የመጀመሪያው አዲ ፓወር ኤግዚቢሽኖችም ዛሬ ይዘጋሉ፡፡  

 የዛምቢያ መንግስት በአገሪቱ የትምህርት ሚኒስቴር ውስጥ በተፈጸመ የ1.6 ሚሊዮን ዶላር ዝርፊያ ላይ ተሳትፈዋል ያላቸውን ከ80 በላይ ባለስልጣናት ከስራ ማገዱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ የትምህርት ሚኒስትር ቪንሰንት ሙዋሌ፤ ተዘርፏል ከተባለው የህዝብ ገንዘብ ጋር በተያያዘ ባለፈው ረቡዕ ለፓርላማ ባቀረቡት ሪፖርት፣ ባልተገባ የፋይናንስ አሰራር ዝርፊያው እንዲፈጸም አድርገዋል የተባሉ ከ80 በላይ ባለስልጣናት ላልተወሰነ ጊዜ ከስራ ገበታቸው እንደታገዱና ጉዳዩ ተጣርቶ ወንጀለኞች ለህግ እንደሚቀርቡ አስታውቀዋል፡፡  
ለልማት የሰጠሁት እርዳታ ለባለስልጣናት የግል ጥቅም መዋሉ አበሳጭቶኛል ያለው የእንግሊዝ መንግስት፣ ጉዳዩ ተጣርቶ ዝርፊያውን የፈጸሙት ባለስልጣናት በህግ እስኪጠየቁና ከሙስና የጸዳ አሰራር እስኪቀየስ ድረስ በአለማቀፍ የልማት ክፍሉ በኩል ለዛምቢያ መንግስት ሲሰጥ ነበረውን እርዳታ ለጊዜው ማቋረጡን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
በዛምቢያ የህዝብን ገንዘብ እየዘረፉና እያጭበረበሩ ለግል ጥቅማቸው የሚያውሉ ባለስልጣናት ቁጥር እየተበራከተ ነው ያለው ቢቢሲ፤ ባለፈው ወር ላይም ለድሃ ዜጎች ድጋፍ የተመደበ 4.3 ሚሊዮን ዶላር ከታለመለት ጉዳይ ውጭ እንዲውል አድርገዋል የተባሉት የአገሪቱ የማህበረሰብ ልማትና ጡረታ ሚኒስትር ኢምሪን ካባናሺ፣ በፕሬዚዳንት ኤድጋር ሉንጉ ትዕዛዝ ከስራቸው መባረራቸውን አስታውሷል፡፡

ባለፈው ረቡዕ በአለማቀፍ ደረጃ የአክሲዮን ገበያ ዋጋ ቅናሽ መከሰቱን ተከትሎ፣ የአለማችን 500 እጅግ ባለጸጋ ቢሊየነሮች በዕለቱ በድምሩ 99 ቢሊዮን ዶላር ያህል ኪሳራ እንዳጋጠማቸው ተነግሯል፡፡
ከአለማችን ባለጸጎች በዕለቱ ከፍተኛውን ኪሳራ ያስተናገዱት የአማዞን ኩባንያ መስራች አሜሪካዊው ቢሊየነር ጄፍ ቤዞስ ሲሆኑ፣ ባለጸጋው ረቡዕ እለት 9.1 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ ኪሳራ እንደደረሰባቸው ብሉምበርግ ዘግቧል፡፡
በአለማቀፉ የአክሲዮን ገበያ ላይ በተከሰተው በዚህ ቀውስ ሳቢያ ከተጣራ ሃብታቸው ከ1 ቢሊዮን ዶላር በላይ የቀነሰባቸው የአለማችን ቢሊየነሮች 17 ናቸው ያለው ዘገባው፤ የአለማችን የቴክኖሎጂው ዘርፍ 67 ባለጸጎችም በድምሩ 32.1 ቢሊዮን ዶላር መክሰራቸውን አመልክቷል፡፡
በአንድ ቀን (ረቡዕ) ቢሊየነሮቿ በከፍተኛ ሁኔታ የከሰሩባት አገር አሜሪካ ናት ያለው ዘገባው፣ የአገሪቱ ቢሊየነሮች በድምሩ 54.5 ቢሊዮን ዶላር መክሰራቸውንም ገልጧል፡፡



    ወላጆቿና ወዳጅ ዘመዶቿ ትዳር እንድትይዝ ነጋ ጠባ መወትወታቸው ያሰላቻት ኡጋንዳዊት የዩኒቨርሲቲ ተማሪ ሉሉ ጀሚማ፤ ከውትወታው ነጻ ለመውጣት በማሰብ ከሰሞኑ ከራሷ ጋር በይፋ ጋብቻ መፈጸሟን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ በፈጠራ ጽሁፍ የሁለተኛ ዲግሪ ትምህርቷን በመከታተል ላይ የምትገኘው ሉሉ ጀሚማ፤ ከሰሞኑ የ32ኛ አመት የልደት በአሏን ባከበረችበት ስነስርዓት ላይ በቬሎ ሽክ ብላ ከራሷ ጋር መጋባቷ ተነግሯል፡፡
ጀሚማ በጋብቻ ስነስርዓቱ ላይ ለታደሙት 30 ያህል እንግዶቿ ባደረገቺው ንግግር፣ የህይወቷ ተቀዳሚ አላማ ትምህርቷን በጥሩ ውጤት ማጠናቀቅና ወደ ስራ ገብታ ውጤታማ ተግባር መፈጸም እንጂ ትዳር መመስረት አለመሆኑን በመግለጽ፣ እንድታገባ የሚወተውቷትን ወላጆቿንና ወዳጅ ዘመዶቿን ለማስደሰት ስትል ከራሷ ጋር ለመጋባት መወሰኗን አስታውቃለች፡፡
“አባቴ ገና የ16 አመት ልጃገረድ እያለሁ ነበር የሰርጌ ዕለት የማደርገውን ንግግር አርቅቆ የሰጠኝ፡፡ እሱም ሆነ እናቴ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ትዳር የምይዝበትን ቀን በመናፈቅ ፈጣሪ ጥሩ ባል እንዲሰጠኝ ሲጸልዩልኝ ነው የኖሩት፡፡ እኔ ግን አላማዬ ትዳር አይደለም” ብላለች ጀሚማ፡፡
ጀሚማ ከራሷ ጋር ለተጋባችበት ሰርግ ያወጣቺው ወጪ፣ በነጻ ወዳገኘቺው አዳራሽ ለሄደችበት ትራንስፖርት የከፈለቺው 2.62 ዶላርና የቬሎ መግዣ ብቻ ነው ያለው ዘገባው፤እምር ድምቅ ያለቺባቸውን ጌጣጌጦች ከእህቷ በውሰት ወስዳ መጠቀሟን፤ የማስዋብና የማሰማመር ሃላፊነቱን አንድ ጓደኛዋ በነጻ እንደከወነችላት፣ ወንድሟ ደግሞ የኬክ ወጪውን እንደሸፈነላት አክሎ ገልጧል፡፡

Sunday, 14 October 2018 00:00

ከመጠምጠም መማር ይቅደም

ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት ባልንጀራዎች ነበሩ፡፡ ወደ አንድ ሩቅ አገር ለመሄድ አስበው መንገድ ጀመሩ፡፡ አንደኛው በሽተኛና ለቋሳ ነው፡፡ ሁለተኛው ብርቱና ጤናማ ሰው ነው። የሚሄዱት በረሀውን አቋርጠው ነው፡፡ ፀሐዩ ያነድዳል፡፡ አሸዋው ያቃጥላል፡፡ በረሀው ረዥምና ሰፊ ነው፤ አቅምና ወኔ ይፈታተናል፡፡ በዋዛ ማለፍ አልተቻለም፡፡
በሽተኛው ተዝለፍልፎ ወደቀ፡፡ ጤነኛውና ጠንካራው፤ በሽተኛውን ከወደቀበት አንስቶ ተሸክሞ፣ በረሀውን እስኪጨርሱ ድረስ ተጓዙ፡፡ አወረደውና ጥቂት አረፍ አሉ፡፡
አየሩ እየቀዘቀዘ፣ ጀንበሯ እያዘቀዘቀች መጣች፡፡ ጥቂት እንደሄዱ “እንተኛ?” አለ በሽተኛው፡፡
“እውነትክን ነው፡፡ በጊዜ መተኛት፣ በጠዋት መነሳት፣ የጤንነት ምንጭ ነው! የጠቢብነት መሰረት ነው፡፡ ሀብትም፡፡”
“Early to bed
and early to rise
makes a man, healthy, wealthy and wise. እንዲሉ ፈረንጆች፡፡” አለ ጤነኛውና በሳሉ ጓደኛው፡፡
ተኙ፡፡
ማታ ነው - የጅብ ሰዓት፡፡ ጅብ፤ ጓደኛሞቹ ወደተኙበት መጣ፡፡ በሽተኛው የጅቡን እንቅስቃሴ ሰምቶ፣ አወቀው፡፡ ስለዚህ ጎኑ ያለውን የበረሀ ጓደኛውን ትቶ ሮጠና ዛፍ ላይ ወጣ፡፡ ጅቡ ወደተኛው ሰው ተጠጋ፡፡ ጆሮው ዙሪያ ተጠግቶ አሸተተውና ምንም ሳያደርገው ሄደ፡፡ ጅብ የሞተ አይነካምና፡፡
 ይህ ሁሉ ሲሆን በሽተኛ ጓደኛው ዛፍ ላይ ሆኖ ቁልቁል ይመለከታል፡፡ ጅቡ ከራቀ በኋላ ከዛፉ ላይ ወረደና ወደ ጓደኛው ሄደ፡፡ ለካ ጓደኛው የጅብን ባህሪ ስለሚያውቅ ነው፣ ፀጥ እረጭ ብሎ የሞተ ያስመሰለው!!
በሽተኛው ጤነኛውን ጠየቀው፡- “ጅቡ አፉን በጣም ጆሮህ ላይ አቅርቦ ምን አለህ?”   
ጠንካራው ሰውም እንዲህ ሲል መለሰ፡-
“ሁለተኛ፤ በክፉ ቀን የሚከዳ ባልንጀራ አትያዝ ብሎኝ ነው ያለፈው!” አለው፡፡
*   *   *
ለካ የሞተ መምሰል አንዳንዴ አሪፍ እስትራቴጂ ነው! ጊዜን የማወቅ ጉዳይ ነው፡፡ መንጋትና መምሸቱን ከማያውቅ ትውልድ ይሰወረን! ከከሀዲም ያድነን!
“ትላንቱን የማያውቅ
ዛሬን የሚያሳስቅ
 ነገን የሚደብቅ
እንደኖረ ሳይሆን እንዳይኖረው ይወቅ” -- ብሏል ገጣሚው ፀጋዬ ገብረመድህን በ”ቴዎድሮስ ስንብት ከመቅደላ ላይ”-  ይህን መሳዩን ትውልድ፡፡
“ሽማግሌውን ባንቀልባ፣ ከምንሸከም እንኮኮ
ጎልማሳውን ከወኔ ጣር፣ ካልፈታን ከፍርሃት ምርኮ”  
እንደ ወዶ ገባ ኮርማ፣
መጠለሉን ከሴት ታኮ
ካቀቃተን ምንድን ነን እኮ?”
 ትውልድን ማዳን ፀጋ ነው፡፡ ጥረታችን እዚያ ዙሪያ ይሁን፡፡ “ወጣት የነብር ጣት” የሁሉም ዘመን ማተብ አይደለም! “የነብርን ጅራት አይዙም፤ ከያዙ ጭራሽ አይለቁም” የሚባለው ለለውጥም ይሰራል፡፡ (ለውጡ ጅራት ይኑረውም አይኑረውም) ለማናቸውም ዓይነት ለውጥ መዘጋጀት፡፡ ከማናቸውም ዓይነት ለውጥ መነሳትና ለማጥበቅ ሀሞትን መሰነቅ እንጂ እህህም እህህም የትም አያደርስምና፡፡ “እህህን ለፈረስ ያስተማርኩ እኔ ነኝ እሱንም ቢርበው እኔን ሲቸግረኝ” (ለመሆኑ እህህ … ምን ያህል ረጅም ነው? ሳንወለድ ጀምሮ ስንሞትም እሱ ቀጣይ ነው?!) Sustainable poverty /ዘላቂ ድህነት/ መኖር አለመኖሩን መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች (NGOs) ይንገሩን፡፡
“ወጣቱማ ይማር! ቢፈልግ ደግሞ ይማረር
ሀሁውን በቅጡ ይቁጠር
ጥቁር መጋረጃ ይቅደድ
ፈተናን መሸሽ ያስወግድ
የልጅነቱን ያህል ይሂድ!
የወጣትነቱን ይንደድ
የጎልማሳነቱን ይውደድ
እንጂ በትኩሳት ብቻ፣ በጀማነትም አይንደድ!
በዚህም በዚያኛውም ስም፣
ትርፍ ፍለጋ አይሰደድ!
ለተሻለ ነገር ሁሉ፣ በራሱ መንገድ ይወደድ!”
ብቻ ለማናቸውም የተሻለች ኢትዮጵያን ለመፍጠር፤ “ከመጠምጠም መማር ይቅደም!!

 በሳምንቱ መጀመሪያ በተካሄደው የአሜሪካን ሚዩዚክ አዋርድ፣ አራት ሽልማቶችን ያገኘቺው ታዋቂዋ አሜሪካዊ ድምጻዊት ቴለር ስዊፍት፣ ያገኘቻቸውን ሽልማቶች 23 በማድረስ፣ በሴቶች ዘርፍ አዲስ ክብረወሰን ማስመዝገቧ ተዘግቧል፡፡ባለፈው ማክሰኞ በተካሄደው አመታዊው አሜሪካን ሚዩዚክ አዋርድ ስነስርዓት ላይ የአመቱ ምርጥ አርቲስትን ጨምሮ በአራት ዘርፎች የዋንጫ ተሸላሚ በመሆን ያገኘቻቸውን ሽልማቶች 23 ያደረሰቺው ቴለር ስዊፍት፤ በዊትኒ ሆስተን ተይዞ የነበረውን ክብረወሰን መስበሯን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ድምጻዊቷ በሎሳንጀለስ የማይክሮሶፍት ቴአትር በተካሄደው የሽልማት ስነስርዓት ላይ ባደረገቺው ንግግር፤ በመጪው ህዳር መጀመሪያ ላይ በሚካሄደው የአሜሪካ የሚድተርም ምርጫ ላይ ዲሞክራቶችን ወክለው ድምጻቸውን እንዲሰጡ ለደጋፊዎቿ ጥሪ አቅርባለች፡፡

   ዱባይ ከቱሪስቶች 29.7 ቢ. ዶላር በማግኘት ቀዳሚ ከተማ ናት


    ለሁለት ተከታታይ አመታት በብዛት በመጎብኘት ከአለማችን ከተሞች ቀዳሚነቱን ይዛ የቀጠለቺው የታይላንድ ርዕሰ መዲና ባንኮክ፣ ዘንድሮም በ20.5 ሚሊዮን አለማቀፍ ቱሪስቶች በመጎብኘት፣ የአንደኛነት ስፍራዋን ማስጠበቋ ተነግሯል፡፡
ማስተርካርድ የተባለው ተቋም ሰሞኑን ያወጣውን የአለማችን የአመቱ ምርጥ የቱሪስት መዳረሻ ከተሞች ሪፖርትን ጠቅሶ ፎርብስ እንደዘገበው፣ ባንኮክ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017 ብቻ በ20.5 ሚሊዮን አለማቀፍ ቱሪስቶች የተጎበኘች ሲሆን ይህ የጎብኝዎቿ ቁጥር በተገባደደው የፈረንጆች አመት 2018 መጨረሻ በ9.06 በመቶ  እድገት ያሳያል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በመላው አለም የሚገኙ 162 ከተሞችን የአመቱ አለማቀፍ የንግድና የቱሪዝም ጎብኝዎች ፍሰት መሰረት አድርጎ ተቋሙ ባወጣው ሪፖርት፣ ከባንኮክ ቀጥሎ ያለውን የሁለተኛነት ደረጃ የያዘቺው የእንግሊዟ ርዕሰ መዲና ለንደን ስትሆን ከተማዋ በአመቱ በ19.83 ሚሊዮን ሰዎች ተጎብኝታለች፡፡
የፈረንሳይ መዲና ፓሪስ በ17.44 ሚሊዮን አለማቀፍ ጎብኝዎች የሶስተኛነት ደረጃን ስትይዝ፣ ዱባይ በ15.79 ሚሊዮን ጎብኝዎች በአራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ሲንጋፖር በ13.91 ሚሊዮን፣ ኒው ዮርክ በ13.13 ሚሊዮን፣ ኳላላምፑር በ12.58 ሚሊዮን፣ ቶኪዮ በ11.93 ሚሊዮን፣ ኢስታምቡል በ10.7 ሚሊዮን፣ ሴኡል በ9.54 ሚሊዮን ሰዎች በመጎብኘት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአምስተኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ መያዛቸውን ዘገባው አስታውቋል፡፡
በፈረንጆች አመት 2017 ከአለማቀፍ ቱሪስቶች ብዙ ገቢ በማግኘት ከአለማችን ከተሞች ቀዳሚነቱን የያዘቺው ዱባይ መሆኗን የጠቆመው ዘገባው፣ ከተማዋ በአመቱ በድምሩ 29.7 ቢሊዮን ዶላር ማግኘቷን አመልክቷል፡፡ ከአለማቀፍ ቱሪስቶች ብዙ ገቢ በማግኘት ሁለተኛ ደረጃን የያዘቺው የሳኡዲ አረቢያዋ መካ በአመቱ በድምሩ 18.45 ቢሊዮን ዶላር ያገኘች ሲሆን  ለንደን 17.45 ቢሊዮን ዶላር፣ ሲንጋፖር 17.02 ቢሊዮን ዶላር፣ ባንኮክ በ16.36 ቢሊዮን ዶላር በቅደም ተከተላቸው እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ መያዛቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡

 የ2019 የፈረንጆች አመት የታይም የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ የእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም የአንደኛነት ደረጃን መያዙ ተዘግቧል፡፡
ሌላው የእንግሊዙ ታዋቂ ዩኒቨርሲቲ ካምብሪጅ የአምና ክብሩን በማስጠበቅ የሁለተኛ ደረጃን ሲይዝ፣ የአሜሪካው ስታንፎርድ አምና በነበረበት ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡ በአመቱ የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ያለውን ደረጃ የያዙት የአሜሪካዎቹ ማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ፣ ካሊፎርኒያ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ፣ ሃርቫርድ፣ ፕሪንሲቶንና የል ሲሆኑ፣ ኢምፔሪያል ኮሌጅ ለንደን ስምንተኛ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቺካጎ አስረኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡
በአመቱ የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝሩ ውስጥ በርካታ ዩኒቨርሲቲዎችን በማስመዝገብ ቀዳሚነቱን የያዘቺው አሜሪካ ስትሆን፣ በዝርዝሩ ውስጥ 172 የአገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች መካተታቸው ተነግሯል፡፡ ጃፓን 103 ዩኒቨርሲቲዎቿን በዝርዝሩ ውስጥ በማካተት የሁለተኛነት ደረጃን ስትይዝ፣ ቻይና በበኩሏ 72 ዩኒቨርሲቲዎቿን በዝርዝሩ አካትታ ሶስተኛነቱን ይዛለች፡፡

 ባለቤታቸው ጠ/ሚ ናጂብ ራዛቅ የተመሰረቱባቸው ክሶች 25 ደርሰዋል

   
   በስልጣን ዘመናቸው ፈጽመዋቸዋል በተባሉ የገንዘብ ማጭበርበርና በስልጣን የመባለግ ወንጀሎች 25 ክሶች የተመሰረቱባቸው የቀድሞው የማሌዢያ ጠቅላይ ሚኒስትር ናጂብ ራዛቅ ባለቤት ቀዳማዊት እመቤት ሮሳማህ ማንሶር፣ 17 የታክስና ገንዘብ ማጭበርበር ክሶች ተመስርቶባቸዋል፡፡
የቅንጦት ኑሮን በመውደድና በሚሊዮን ዶላሮችን እያወጡ በውድ ጌጣጌጥ በማሸብረቅ የሚታወቁት የቀድሞዋ ቀዳማዊት እመቤት ሮሳማህ ማንሶር፣ ረቡዕ በአገሪቱ የጸረ ሙስና ተቋም ሃላፊዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውንና ከትናንት በስቲያ በኳላላምፑር ፍርድ ቤት መቅረባቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የ66 አመቷ ሮሳማህ ማንሶር ፍርድ ቤት ቀርበው በሰጡት ምላሽ፣የተከሰሱባቸውን ሁሉንም የወንጀል ድርጊቶች አለመፈጸማቸውን ገልጸው፣ ክሶቹን መቃወማቸውንና የዋስ መብታቸው እንዲከበርላቸው መጠየቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ፍርድ ቤቱም በግማሽ ሚሊዮን ዶላር  ዋስትና ከእስር እንዲለቀቁ መፍቀዱን አመልክቷል፡፡
በብዙ ሚሊዮን ዶላሮች የሙስና ቅሌት 21 የወንጀል ክሶች ተመስርቶባቸው የነበሩት የቀድሞው የማሌዢያ ጠቅላይ ሚኒስትር ናጂብ ራዛቅ፤ ባለፈው ሳምንት 556 ሚሊዮን ዶላር የህዝብ ገንዘብ ያለ አግባብ ወደ ግል ካዝናቸው ከማስገባታቸውና በስልጣን ከመባለጋቸው ጋር በተያያዘ፣ አራት አዳዲስ ክሶች እንደተመሰረቱባቸው  ተዘግቧል፡፡