Administrator

Administrator

  የቀድሞ የህፃናት አምባ ውስጥ አድገው በተለያዩ የስራ መስክ በተሠማሩ ግለሠቦች የተቋቋመው ‹‹ትምህርት ለተቸገሩ በጎ አድራጎት ማህበር›› መጋቢት 10 ቀን 2009 ዓ.ም የገቢ ማሠባሠቢያ ፕሮግራም ያካሂዳል፡፡
ከ3 መቶ በላይ የትምህርት እድል ማግኘት ያልቻሉ ህፃናትን በኮተቤ ኪዳነምህርት ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በከፈተው ትምህርት ቤት በማስተማር የሚታወቀው ማህበሩ፤ በአሁኑ ወቅት ይህን በጎ ተግባር ለማከናወን የአቅም ውስንነት ስላጋጠመው የእርዳታ ማሠባሠቢያ መርሃ ግብር ለማዘጋጀት መገደዱን አስታውቋል።
በዚህም መሰረት መጋቢት 10 ቀን 2009 ዓ.ም ከላምበረት አዲሱ መናኸሪያ ተነስቶ እስከ ኮተቤ ኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን የ3.5 ኪሎ ሜትር የእግር ጉዞ በማዘጋጀትና የሙዚቃ ዝግጅትን አካቶ የገቢ ማሠባሠቢያ ሰፊ ፕሮግራም እንደሚያደርግ አስታወቆ፤ በእለቱ ድጋፍ እንዲደረግለት ጥሪ አድርጓል፡፡

 በጅማ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ኮሌጅ የ2ኛ ዓመት የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተማሪ፣ የሆነው ወጣት በአንገት ማዕተብ ጉዳይ ከመምህሩ ጋር ተጋጭቶ “የትምህርት ውጤቴ ተበላሸ” በሚል ራሱን አጠፋ፡፡
ተስፋዬ ገመዳ የተባለው ተማሪ የስነ ልቦና ሳይንስ መምህሩ በቡድን ያዘዙትን አሳይመንት ስራ አዘጋጅቶ በመድረክ ላይ ሊያቀርብ ሲል መምህሩ፣ “በአንገትህ ላይ ያደረከውን ማተብ ወይ አውልቅ ወይም ሸፍነው” ሲሉት ተማሪው፤ “ይህ የእምነቴ መገለጫ ነው፤ ያዘዙኝን ማድረግ አልችልም” የሚል ምላሽ እንደሰጣቸውና መምህሩም “ያዘዝኩህን ማድረግ ካልቻልክ የሰራኸውን ማቅረብ አትችልም” በማለታቸው ስራውን ሳያቀርብ መቅረቱንና ከመድረኩ ወርዶ በእጁ የያዘውን የቡድን  ስራ ሪፖርት በንዴት ቀዳዶ መቀመጡን የአይን እማኞች አስታውሰዋል፡፡ በወቅቱ ተማሪው ክፍለ ጊዜውን አቋርጦ ከክፍሉ መውጣቱንና ተመልሶ  ሊገባ ሲል መምህሩ አትገባም ብለው እንደከለከሉትና፣ ተማሪውም ስሜታዊ ሆኖ ከመምህሩ ጋር ለፀብ መጋበዙን፣ ተማሪዎችም በመሃል ገብተው እንደገላገሏቸውና የአካዳሚክ ዲኑ በቦታው ተገኝተው ስለተፈጠረው ችግር ተማሪዎችን በመጠየቅ፣ ፀቡን ማረጋጋታቸውን ተማሪዎች ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡
በሌላ ቀን እንደተለመደው ተማሪው የስነልቦና ክፍለ ጊዜ ትምህርቱን ለመከታተል ወደ ክፍል ሲገባ መምህሩ በድጋሚ ከክፍል እንዳስወጡት፣ ተማሪውም ለአካዳሚክ ዲኑ አቤቱታ ማቅረቡንና ዲኑም የትምህርቱ የመጨረሻ ክፍል ጊዜ ስለሆነ ‹‹በቃ ተወው በውጤትህ ላይ ምንም ለውጥ አያመጣም›› ብለው አረጋግተው እንደሸኙት፣ የተማሪው የቅርብ ጓደኞች ገልፀዋል፡፡
በኋላም ፈተና እንዲወስድ የተፈቀደለት ሲሆን የተለጠፈውን የፈተና ውጤት ሲመለከት ግን “No Grade” (ምንም ውጤት የለም) የሚል ስለነበር ወዲያው በንዴት ወደ ተከራየበት ቤት በማምራት የዚያኑ እለት ራሱን ግቢ ውስጥ ባለ የማንጎ ዛፍ ላይ  ሰቅሎ ማጥፋቱን የቅርብ ጓደኞቹ ገልፀዋል፡፡
ፖሊስና የአካባቢው ህብረተሰብ በቦታው ደርሶ ከተሰቀለበት ሲያወርዱት ነፍሡ ከስጋው  እንዳልተላቀቀችና ወደ ሆስፒታል በመሄድ ላይ ሣለ ህይወቱ ማለፉን የጠቆሙት ምንጮች፤ የቀብር ሥነስርዓቱም ከትናንት በስቲያ በትውልድ አካባቢው በሰሜን ምዕራብ ሸዋ፣ ደገሞ ወረዳ መፈፀሙን ለማወቅ ተችሏል፡፡
አስከሬኑን ለቤተሰብ ያደረሱት መርማሪ ፖሊስ ዮሐንስ መገርሳ፤ ተማሪው ከመምህሩ ጋር በመጣላቱ ራሱን  እንዳጠፋ ጥርጣሬ መኖሩንና የሆስፒታል የምርመራ ውጤት በማስረጃነት እየተጠበቀ መሆኑን ጠቁመው፣ ጉዳዩ ገና በመጣራት ላይ ነው ብለዋል - ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፡፡

 ከቻይና ስመ-ጥር የጫማ አምራች ኩባንያዎች አንዱ የሆነውና ከአምስት አመታት በፊት በኢትዮጵያ ፋብሪካውን ከፍቶ የማምረት ስራ የጀመረው ሁጂያን ግሩፕ፤ ኢንቨስትመንቱን ለማስፋፋትና ለ100 ሺ ሰዎች ተጨማሪ የስራ ዕድል ለመፍጠር ማቀዱን አስታወቀ፡፡
ሁጂያን ግሩፕ ለ6 ሺህ ያህል ኢትዮጵያውያን ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠሩንና ለአገሪቱ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘት ረገድ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ያስታወሱት የኩባንያው ፕሬዚዳንት ዣንግ ሁዋሮንግ፤ 100 ሺህ ያህል አዳዲስ የስራ ዕድሎችን የመፍጠርና ካፒታሉን ወደ 10 ቢሊዮን ዶላር የማሳደግ ዕቅድ እንዳለው መግለጻቸውን ፒፕልስ ዴይሊ ድረገጽ ዘግቧል፡፡
ኩባንያው በኢትዮጵያ በከፈተው ፋብሪካ እያመረተ ለውጭ ለገበያ የሚያቀርባቸው የጫማ ምርቶች፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ልጅ የሆነቺው ኢቫንካ ትራምፕ ያቋቋመቺውን ኢፖኒመስ የተባለ ኩባንያ ጨምሮ በበርካታ የአውሮፓ አገራት ኩባንያዎች ዘንድ ተወዳጅነት ማትረፋቸውንም ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡

 ጥልቅ ሀዘን እንደተሰማቸው ለፍ/ቤቱ ተናግረዋል
                                      
       ህገ መንግስታዊ ስርአቱን በኃይል ለማስወገድ ሙከራ አድርገዋል እንዲሁም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ድንጋጌዎች ተላልፈዋል በሚልና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ክስ የተመሰረተባቸው ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ ለፍ/ቤት ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄ ተቀባይነት አላገኘም፡፡
አንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር መረራ ጉዲና የካቲት 24 ቀን 2009 ዓ.ም በነበራቸው ቀጠሮ፣ የተከሰሱት በወንጀል ህጉ ስለሆነና ተከሳሹ ከዚህ ቀደም የነበራቸው የፖለቲካ ታሪክ፣ ከቤልጂየም ሲመለሱ እንደሚታሰሩ እየተነገራቸው እንደመጡና ከሀገር የመኮብለል ፍላጎት የሌላቸው መሆኑ ታይቶ እንዲሁም የስኳር ህመምተኛ በመሆናቸው በዋስትና ሆነው ጉዳያቸውን እንዲከታተሉ እንዲፈቀድላቸው ጠይቀው እንደነበር ይታወሳል፡፡
አቃቤ ህግም የተጠረጠሩበት ወንጀል ህገ መንግስታዊ ስርአቱን በኃይል የመናድ ሙከራ በመሆኑ በዋስትና ቢወጡ መረጃ ሊያሸሹ ይችላሉ በሚል የዋስትና ጥያቄው ውድቅ እንዲደረግለት ጠይቋል፡፡
የግራ ቀኙን አስተያየት የመረመረው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት፤ ተጠርጣሪው በተከሰሱበት የህግ አንቀፅ ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ ከ15 ዓመት በላይ ወይም በእድሜ ልክ አሊያም በሞት ሊያስቀጣ የሚችል በመሆኑ ዋስትናውን ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡
በችሎቱ ማጠናቀቂያ ላይ ዶ/ር መረራ የምናገረው አለኝ ብለው ሲፈቀድላቸው፡-
“ከእነ ጀነራል መንግስቱ ነዋይና ጀነራል ታደሰ ብሩ ዘመን ጀምሮ ከአንድ ትውልድ በላይ ገዳዮችና ሟቾች፣ ታሳሪዎችና አሳሪዎች በበዙበት የሀገራችን የፖለቲካ ድራማ ውስጥ በመቆየት አንድ ከሆዱ በላይ ለሀገሩ የሚያስብ ምሁር ማድረግ እንዳለበት ሁሉ፣ ከአርባ አምስት አመታት በላይ ለሀገሩ የተሻለ ለውጥ እንዲመጣ በታማኝነት መታገሌ እየታወቀ ወደ ጎን መገፋቴን፤ ለሁላችንም የምትሆንና በእኩልነት የምታስተናግደን ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እንድትፈጠርና ነፃ የፍትህ ስርአት በሀገራችን እንዲሰፍን ላለፉት 25 ዓመታት በመታገሌ መከሰሴ አንሶ የሀገሪቱ ፓርላማ አባል ጭምር የነበርኩት ሰው፣ ለተራ ወንጀለኛ የሚፈቀድ የዋስ መብት በመከልከሌ የተሰማኝን ጥልቅ ሀዘን ለራሴ ብቻ ሳይሆን እኛም ሆንን ልጆቻችን በሰላም ይኖሩበታል በምንለው መከረኛ ሀገራችንና አላልፍለት ብሎ ለታመሰው ለመላው መከረኛ ህዝባችን ጭምር መሆኑ እንዲታወቅልኝ ነው” የሚል ንግግር አድርገዋል፡፡

Saturday, 11 March 2017 12:53

መጫወቻ ፍለጋ

የሠፈር ልጆች ቅዳሜ-ቅዳሜ መጫወቻ ፍለጋ ዙረት እንሔድ ነበር፡፡ ብዙውን ጊዜ ምርጫችን ፈረንጆች ቤት ጓሮ ማንጎዳጎድ ነበር፡፡ ፈረንጆቹ ከቤታቸው አጥር ግቢ ውጪ ጉድጓድ ቆፍረው ቆሻሻውን እዚያ ይጥሉታል፡፡ ዘበኞቻቸውም ጠቃሚ የሆነውን ዕቃ ይቃርማሉ፡፡ በተቀረው ላይ እሳት ለኩሰው ይለቁበታል፡፡ አንዳንዴ ከመቃጠሉ በፊት ደርሰን ደጋግ ዘበኞች ካጋጠመን ደስ ያለንን ዕቃ እንወስዳለን፡፡ ግን ብዙውን ጊዜ የሚያጋጥሙን እርጉም ዘበኞች ስለነበሩ ያባርሩናል፡፡ ሸሽተን ከሌላ ቪላ ቤት ጓሮ ፍለጋችንን እናጧጡፋለን፡፡
ከዕለታቱ በአንዱ ቀን ብትንትኗ የወጣ አሻንጉሊት አገኘን፡፡ ቀጢሳው ከትከሻዋ እስከ ዳሌዋ ያለው የአሻንጉሊቷን አካል ሲያገኝ “ባትጋሩኝ! በትኩስ እንጀራ በመርፌ ቀዳዳ!” ብሎ ጮኸ፡፡
አሻንጉሊቷ ጭንቅላት፣ እጅና እግር እንደሌላት ካስተዋለ በኋላ “በእናታችሁ ልጆች! የተቀረውን አካሏን ካገኛችሁት ትሰጡኛላችሁ? የአሻንጉሊቷ ሙሉ አካል ከተገኘ ልብስ ሰፍተንላት ሁላችንም እንጫወትባታለን፡፡” አለ ቀጢሳው እየተለማመጠን።
ብዙም ሳይቆይ ኃይሉ ዶሮ “ባትጌ!” አለና ጮኸ። የአሻንጉሊትዋን እጆች ሽቅብ እንደ ዋንጫ ሰቅሎ እያሳየን፡፡
“ለቀጢሳው ስጠው!” እያልን ሁላችንም ለመነው፡፡ ሰጠው፡፡
“ዶሮ ደግ ልጅ ነው” አልን ሁላችንም፣ ቆሻሻውን ማገለባበጡን እየቀጠልን፡፡
የቆሻሻው ትንፋግ አይነሳ! አዋቂን ሰው ከአገር ያስለቅቃል፡፡ እኛ ግን መጫወቻው በልጦብን ያንን ክርፋት የልጅነት አፍንጫችን ችሎታል፡፡
ከጥቅም ውጭ የሆኑ የሕክምና ዕቃዎች፣ የምግብ ማሸጊያ ፓኮዎች፣ ቆርቆሮዎች፣ አርተፊሻል ፀጉር፣ የፀጉር ማስያዣ፣ ካርቶኖች፣ ፊኛዎች አገኘን። ፊኛውን እየተቀባበልን ነፋነውና ተጫወትንበት፡፡ (በበኋለኛው የሕይወት ዘመኔ ፊኛ እያልን ስንነፋው የነበረው ኮንዶም እንደነበረ ተገንዝቤያለሁ፡፡)
እዚያው ትንፋጉ ላይ ሆነን አስቂኝ ትዕይንት እየሰራን ያንን መራር ሕይወት እናጣፍጠው ነበር፡፡ ቀጢሳው ግማሽ ጎኑ የተቃጠለውን አርተፊሻል ፀጉር አናቱ ላይ አድርጎ፣ የተሰበረ የፀጉር ጌጥ ሰክቶበት እንደ ፈረንጅ ኮረዳ እየተሽኮረመመ “ዊስ ዋይስ” ብሎ በራሱ እንግሊዝኛ ተናገረ፡፡
ጎቢጥ ያንን አንድ ዓይኑ ላይ መስታወት የሌለውን መነፅሩን አደረገና አፉ ላይ የሲጋራ ቁራጭ ወትፎ እንደ ፈረንጅ ጎረምሳ ጎርነን ባለ ድምፅ፤ “ዋት ኢዝ ዊስ ዋይ?” አለ በብረት ዘንግ ቆሻሻውን እየቆፈረ፡፡ የአሻንጉሊትዋን እግሮች አገኘ፡፡ ለቀጢሳው ሰጠው።
ቀጢሳው ቻርሊ ቻፕሊን ፊልም ላይ ባየነው ስልት በደስታ ተውረግርጎ ሹል አፉን አሞጠሞጠና ሲሳይ ጎቢጥን ሳመው፡፡
ፍለጋችን ቀጠለ፡፡ ውሮ አንድ ነገር ደብቆን ኪሱ ሲከት ሴምላል አየውና፤ “ምን አገኘህ?” ሲል ጠየቀው፡፡ ሁላችንም ካቀረቀርንበት ቀና አልን፡፡ ውሮ ቁንጮውን እያከከ “ምንም አላገኘሁም!” አለ፣ ኪሱን ጨብጦ ላለማስፈተሽ እየሞከረ፡፡
“እስኪ እናቴ ትሙት በልና ማል?!” ሲል ሴምላል ንፍጡን ሽቅብ እየሳበ ጠየቀው፡፡ ውሮ መማሉን ፈራ፡፡ በዚህ ምልልስ ወቅት መኩዬ ቀጫጫው እንደ እባብ ተስባ ከውሮ ኋላ ደርሳ ከኪሱ በፍጥነት አንድ ነገር ስትስብ የአሻንጉሊቷ ጭንቅላት መሬት ዱብ አለ፡፡
“ወይኔ አሻንጉሊቴን!” ሲል ውሮ ጩኸቱን አቀለጠው፡፡ መኩዬ ቀጫጫው የአሻንጉሊት ጭንቅላት ከመሬት አንስታ እየደባበሰች ለቀጢሳው እንዲሰጠው ለመነችው፡፡
ውሮ “እምቢ” አለ፡፡
ሁላችንም ብንለምነው ችክ አለ፡፡ እርሱም የራሱ አሻንጉሊት እንዲኖረው፣ የተቀረውን አካል በሽቦና በጨርቅ ሠርቶ ሊጫወትበት መፈለጉን በልቅሶ ዜማ አወራን፡፡ በዚህ ራስ ወዳድነቱ ሁላችንም አኮረፍነው፡፡ መኩዬ ቀጫጫውም የአሻንጉሊቷን ጭንቅላት አፍንጫው ላይ ወረወረችለት፡፡
(“ልጅነት” ከተሰኘው የደራሲ ዘነበ ወላ
መፅሀፍ ላይ የተቀነጨበ)

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ - ዓይነ - ሥውር እናት የነበረችው አንድ ልጅ ነበረ፡፡ ይሄ ልጅ እናቱን አደባባይ ማውጣት አይፈልግም፡፡ ያፍርባታል፡፡ በሄደበት ቦታ ሁሉ ሌሎች ልጆች ስለ እናታቸው ሲያወሩ፣ እሱ አያወራም፡፡ ሌላው ቀርቶ ሌሎቹ ስለ እናታቸው ደግነት ሲያወሩ እሱ እናቱን አያነሳም። እናቱ በእናትነቷ እስክትሸማቀቅና እስክትሸሸግ ድረስ በሰፈር ልጆች መሳቂያ መሳለቂያ እንድትሆን አደረጋት፡፡
በትምህርቱ እየገፋ ታዋቂ ልጅ እየሆነ ሲሄድ፣ ስለ እናቱ መናገሩን ጨርሶ ተወ - ያለ እናት የተወለደ እስኪመስል ድረስ፡፡ ውጪ አገር ሄዶ አድጎ ተመንድጎ፣ አንቱ ተብሎ ትልቅ ስራ ያዘ፡፡ እናቱን ረሳት፡፡ እናቱን የከዳና የናቀ መሆኑን ግን የሚያውቅ ማንም የለም፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ትውልድ አገሩ ውስጥ ለሚደረግ ትልቅ ኮንፈረንስ ተጋበዘና ወደ ሀገሩ መጣ፡፡
ስብሰባው ሲያበቃ እስከ ዛሬ ረስቷት የነበረችውን እናቱን እስቲ ከመጣሁ አይቀር ልያት ብሎ ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ቤት ግን የጠበቀችው እናቱ ሳትሆን፣ የእናቱ ታናሽ እህት፣ አክስቱ ናት፡፡
“እናቴስ ወዴት አለች?” አለና ጠየቀ እንደደረሰ፡፡
አክስቱም፤ “እናትህ የለችም?”
ልጅ፤ “ወዴት ሄደች?”
አክስት፣ “ወደማይቀረው አለም”
ልጁ ያልጠበቀው ነበረና ድንጋጤ ላይ ወደቀ፡፡ አለቀሰ፡፡
ሲረጋጋ፤ “እናትህ ከመሞቷ በፊት ‹ድንገት ልጄ ከመጣ ይሄን ደብዳቤ ስጪልኝ› ብላለች፡፡ እንካ ውሰደው” ብላ አክስቱ ትሰጠዋለች፡፡
ሲፈራ ሲቸር እጁ እየተንቀጠቀጠ ይቀበላትና ደብዳቤውን ከፍቶ ያነበዋል፡፡ እንዲህ ይላል፡-
“ልጄ! አንድ ልጄ ሆይ!
ብትገፋኝም፣ ብትርቀኝም፣ ብትንቀኝም ብታስንቀኝም፣ ብትጠላኝም፣ ብታስጠላኝም፣ ብታኮርፈኝም፣ ሰዎች እንዲያፍሩብኝ ብታደርግም፣ አሁንም ያው አንድ ልጄ ነህ! ህይወቴ ከማለፉ በፊት አንድ ነገር ልነግርህ እፈልጋለሁ፡-
ወጣት ሆነህ አንድ ዐይንህን ክፉኛ ያምህ ነበር፡፡ ሐኪም ቤት ወስጄህ ዶክተሩ ዐይንህ ሊጠፋ እንደሚችልና በቀዶ - ጥገና ሌላ ዐይን ካልተተከለልህ ተስፋ እንደማይኖርህ፣ ጨርሶም እንደሚጠፋ፣ ነገረኝ፡፡ የአንተ፣ የነገ ተስፋዬ፣ ገና ብዙ ማየት ያለብህ አንድ ልጄ፤ ዐይንህ - ብርሃንህ ከሚጠፋ የእኔ ዐይን ይጥፋ፤ ብዬ፣ የእኔ ዐይን ይጥፋና አንተ ብርሃን ይኑርህ ብዬ፣ ዐይኖቼን አስወልቄ ላንተ አስተከልኩልህ!! ዛሬ አንተ ሁለት ዐይን የኖረህና እኔ ዐይነ - ስውር የሆንኩት ለዚህ ነው! እይበት! ሰው ሁንበት ብዬ ነው!”
ልጅ በእጁ ይዞ የቀረው ፀፀትን ብቻ ነው!
*   *   *
እናትየውን ኢትዮጵያን አድርገን ብናይ ብዙ ነገር እንማራለን! የዛሬው ትውልድ ከላይ እንደተጠቀሰው ወጣት እንዳይሆን እንመኛለን፡፡
ዛሬም ወጣቱ የማያፍርበት አገር እንዳለው ልናሳውቀው ይገባል፡፡ ከራስ ወዳድነት የፀዳች አገር እንዳለችው በኩራት ማሰብ ይገባዋል፡፡ ጽጌረዳ ያለ እሾክ እንደማትኖር ልብ ይል ዘንድ ልንመክረው ይገባል!
ድርቅ እና የኑሮ ውድነት ዛሬም ከጫንቃችን ላይ አልወረዱም! “የደመናው ሎሌ” የሚለውን ግጥም ያስታውሰናል፡-
ለወትሮው ደመና ፊቱ እየጠቆረ
ዐይኖቹን አሻሽቶ ያነባ ነበረ
    ይዘንብ ነበረ
የዘንድሮ ሰማይ ፈጋግ ሰማያዊ
መልኩን አሳምሮ
ስንቱን ፈጀ በላ ከራብ ተመሳጥሮ
የምድር ከርስ አረረ
አገር ጦም አደረ
ሰው ምጡ ጠናና
ዐይኖቹን አቀና
እንዲሁ ከርተት ከርተት ሰማይ ለሰማይ
ውሃ የለሽ ህዋ ጠብታ-አልባ ጠፈር
ሰማይ አይታረስ በዐይን ብሌን ሞፈር
የዳመናው ሎሌ የዳመናው አሽከር
የዕለት ግብሩ ሆነ ጦም ውሎ ጦም ማደር
ዕንባውን እረጫት ሽቅብ ወደ ላይ ድንገት
ዝናብ ሆና ትወርድ ይሆን ወይ?!
ታህሣሥ 1977 ዓ.ም
(ለ1977 ድርቅ)
የመንግስት ሠራተኞች የተጨመረውን ደሞዝ መሰረት ያደረገ የነጋዴዎች የሸቀጥ ዕቃ ዋጋ መጨመር፤ ሌባና-ፖሊስ ጨዋታ አስገራሚ ነው! ህዝብና ነጋዴ አይጥና ድመት ሆነው መኖር የለባቸውም! ውስጠ-ነገሩ የሀገራችንን ነገር፣ የሀገራችንን የፖለቲካ ሂደት፣ የየትውልዱን ማንነትና የፖለቲካ ተዋንያን ከእናት አገራቸው ጋር ያላቸውን ትሥሥር ሊያመላክተን የሚችል ነው፡፡ መልካም-ትውልድ የመሠረቱን አይረሳም፡፡ ሰፊውን የሀገሩን ሥዕል በሆደ ሰፊነት ያስተውላል፡፡ ከሀገር በፊት የሚመጣን ራስ ተኮርና ራስ ጠቀም አካሄድ ያስወግዳል፡፡ ከእርስ በእርስ መናቆርና መወጋገዝ፤ ከእኩይ ሙግት፣ ከእኔ ልግዘፍ ፖለቲካ፣ ከቀረርቶና ከሜዳሊያ ፍለጋ ሩጫ ራሱን ያገልላል ‹‹ከወጡ ሳይወጠወጥ ወስከንባዩ ፍጥጥ›› ጨዋታ ራሱን በጊዜ ይገላግላል!
መጪው ትውልድ አርአያ ይሻል! አርአያ ልንሆነው ልባችን ይሙላ፣ ሁሉን ነገር ለመንግስት ጥለን አንችለውም! መንግሥት ያለውን ቢል ህዝብ እንደምን ተቀበለው ብሎ ጥናት ማካሄድ የነገራችን ሁሉ አልፋ- ኦሜጋ ነው፡፡ መንግሥት ሊሣሣት ይችላል፡፡ ማረሚያ ነጥቦቹ (Check-points) እኛ ነን!
ተሳስተሃል አቅጣጫህን ቀይር ማለት ኃላፊነታችን ነው (We are the watch-dogs) ይላሉ ፈረንጆቹ እንጂ ተረቱ እንደሚለው፤ ‹‹ንጉሥ የቆረጠው እጅ እንዳለ ይቆጠራል›› እያልን ብዙ አንራመድም! በቀናነት ዕድሜውን ይስጠን!!

አሜሪካ በአመቱ የምትቀበላቸው ስደተኞች ቁጥር ከ110 ሺህ ወደ 50 ሺህ ዝቅ ተደርጓል

        የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ፤ የሙስሊም አገራት ዜጎችን ተጠቂ ያደረገ ነው በሚል አለማቀፍ ተቃውሞ በገጠመውና ከአንድ ወር በፊት ባወጡት የጉዞ ገደብ ላይ የተወሰነ ማሻሻያ በማድረግ ባለፈው ሰኞ ይፋ ያደረጉት አዲሱ የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ፣ ከአገራትና ከተመድ ተቃውሞ እንደገጠመው እየተዘገበ ነው፡፡
የሱዳን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ሱዳናውያን በአሜሪካ በተካሄዱ የሽብር ወንጀሎች ላይ ተሳትፈው እንደማያውቁ በማስታወስ፣ በመጪው ሳምንት ተግባራዊ ይደረጋል ተብሎ በሚጠበቀውና ለሶስት ወራት ይቆያል በተባለው በዚህ የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ ከልብ ማዘኑን መግለጹን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የአሜሪካ መንግስት ሱዳንን ሽብርተኝነትን ይደግፋሉ በሚል ከዘረዘራቸው አገራት ተርታ ማሰለፉን ያስታወሰው ሚኒስቴሩ፤ ሱዳንን ከዝርዝሩ እንዲያወጣ በድጋሚ መጠየቁንም ዘገባው ገልጧል።
አዲሱ የሶማሊያ ፕሬዚዳንት ሞሃመድ አብዱላሂ ሞሃመድ ፎርማጆ በበኩላቸው፣ አሜሪካ የጉዞ ገደቡን እንድታነሳ የጠየቁ ሲሆን፣ የጉዞ ገደቡ በቀጥታ ተጠቂ ከሚያደርጋቸው በርካታ ቁጥር ያላቸው ስደተኞች መካከል፣ በኬንያው ዳባብ የስደተኞች መጠለያ ውስጥ ሆነው ወደ አሜሪካ የሚገቡበትን ቀን በጉጉት በመጠባበቅ ላይ የሚገኙ 15 ሺህ ያህል ሶማሊያውያን ስደተኞች ቀዳሚነቱን እንደሚይዙ ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
በአሜሪካ የሚገኙ 150 ሺህ ያህል ሶማሊያውያን ስደተኞች ለአገሪቱ ኢኮኖሚ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ጉልህ አወንታዊ ሚና እየተጫወቱ ይገኛሉ ያሉት ፎርማጆ፤ አገራቸው አልሻባብን የመሳሰሉ አሸባሪ ቡድኖችን በመዋጋት ረገድ የጀመረቺውን ጥረት አጠናክራ እንደምትቀጥል በመግለጽ፣ የጉዞ ገደቡ ይህን እውነታ ከግምት ውስጥ ያላስገባ ነው ሲሉ ተችተውታል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ፣ ስደተኞች በአገራቸው የገጠሟቸውን መከራና ስቃዮች ለማምለጥ አገራቸውን ጥለው ለመውጣት የተገደዱ ዜጎች እንጂ ወንጀለኞች አይደሉም፣ የትራምፕ ትዕዛዝ ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡
የሃዋይ ግዛት አስተዳደር የትራምፕ የጉዞ ገደብ እንዳይተገበር የሚጠይቅ ክስ ባለፈው ማክሰኞ መመስረቱንና የእስልምና እምነት ተከታዮች የሆኑ ሁለት የአሜሪካ ኮንግረስ አባላትም የጉዞ ገደቡ ሙስሊሞችን ታላሚ ያደረገ አግላይ እርምጃ መሆኑን በመግለጽ፣ ትዕዛዙ ተግባራዊ እንዳይደረግ ተግተው እንደሚታገሉ ማስታወቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ትራምፕ ከዚህ ቀደም ባወጡትና ተግባራዊ እንዳይደረግ በፍርድ ቤት ውሳኔ በታገደው የጉዞ ገደብ ትዕዛዝ ውስጥ ዜጎቻቸው ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ የተከለከሉት አገራት ኢራን፣ ሶማሊያ፣ ሱዳን፣ የመን፣ ሶርያ፣ ሊቢያ እና ኢራቅ እንደነበሩ ያስታወሰው ዘ ጋርዲያን፣ ትራምፕ በአዲሱ ትዕዛዝ ኢራቅን ከዝርዝሩ ማውጣታቸውን ዘግቧል፡፡
በአዲሱ ትዕዛዝ ለውጥ ከተደረገባቸው ጉዳዮች መካከል፣ የስድስቱ አገራት ዜጎች የሆኑ ቋሚ ነዋሪዎች፣ ቪዛ ያላቸው፣ ከዚህ ቀደም በስደተኝነት የተመዘገቡ ወይም ጥገኝነት የተሰጣቸው እንዲሁም ሁለተኛ ዜግነት ያላቸው ሰዎች የጉዞ ገደቡ ሳይመለከታቸው ወደ አሜሪካ መግባት እንዲችሉ መፍቀዱ ይጠቀሳል፡፡
የአሜሪካ መንግስት በአዲሱ የፈረንጆች አመት 2017 ብቻ 110 ሺህ ያህል ስደተኞችን ለመቀበል አቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ አዲሱ የትራምፕ የጉዞ ገደብ ግን በአመቱ ወደ አሜሪካ የሚገቡ የተለያዩ አገራት ስደተኞች ቁጥር ከ50 ሺህ መብለጥ እንደሌለበት የሚያግድ እንደሆነ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

የዘንድሮው የአለም የሴቶች ቀን ከዚህ በፊት ባልተለመደ ሁኔታ የሴቶች መብቶች እንዲከበሩና በሴቶች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶች እንዲቆሙ በሚጠይቁ እጅግ በርካታ ሴቶች የተሳተፉባቸው አድማዎችና የተቃውሞ ሰልፎች በአለም ዙሪያ በሚገኙ የተለያዩ አገራት ከተሞች ባለፈው ረቡዕ ተከብሮ ውሏል፡፡
በዕለቱ በማድሪድ ከ40 ሺህ በላይ ሴቶች አደባባይ ወጥተው የመብት ጥሰቶች እንዲቆሙ በተቃውሞ ሰልፍ የጠየቁ ሲሆን፣  ከአስር ሺህ በላይ የቱርክ ሴቶችም በመዲናዋ ኢስታንቡል ባደረጉት ሰልፍ “ወንዶች በሴቶች ላይ የሚፈጽሟቸው ጾታዊ ጥቃቶች ያብቁ” ሲሉ ድምጻቸውን አሰምተዋል፡፡
በአሜሪካ አንዳንድ ከተሞች “አንድ ቀን ያለ ሴት” የሚል መሪ ቃል ባለው አድማ፣ በርካታ ሴቶች በዕለቱ ከስራ ገበታቸው በመቅረት የሴቶችን ሚና ለማሳየት የሞከሩ ሲሆን ኒውዮርክንና ዋሽንግተንን ጨምሮ በተለያዩ የአገሪቱ ከተሞች በሺዎች የሚቆጠሩ ሴቶች የአለም የሴቶች ቀንን ምክንያት በማድረግ ሰልፍ እንደወጡ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
አየርላንዳውያን ሴቶች በበኩላቸው፤ ውርጃን የሚከለክሉ የአገሪቱ ህጎችን በመቃወም ከስራ የማቆም አድማ ከማድረግ ባለፈ ቀኑን ሙሉ ጥቁር ልብስ ለብሰው ውለዋል፡፡ የፖላንድ ሴቶች የእግር ጉዞ በማድረግ መንግስታቸው የጾታ እኩልነትን እንዲያሰፍንና ጥበቃ እንዲያደርግ የጠየቁ ሲሆን፣ ለሴቷ ተገቢው ክብር እንዲሰጣትም ድምጻቸውን አሰምተዋል፡፡
ከመቼውም ጊዜ በተለየ በበርካታ የአለማችን አገራት ከተሞች ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሴቶች ለመብቶቻቸው መከበር አደባባይ በስፋት በመውጣት ድምጻቸውን ያሰሙበት ነው በተባለው በዘንድሮው የአለም የሴቶች ቀን፤ በሜክሲኮ፣ በፖላንድ፣ በኬንያ፣ በጀርመን፣ በዩክሬን፣ በየመንና በሌሎች የአለማችን አገራት የተለያዩ ሰልፎች፣ አድማዎችና ተቃውሞዎች ተከናውነዋል፡፡

 የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በምስራቅ አፍሪካ በሚገኙ ዘጠኝ አገራት በድምሩ ከ17 ሚሊዮን በላይ ሰዎች የርሃብ አደጋ እንደተጋረጠባቸው ማስታወቁን ቪኦኤ ዘግቧል፡፡ የተመድ ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ፤ ሶማሊያና
ደቡብ ሱዳንን ጨምሮ በአካባቢው በሚገኙ ዘጠኝ አገራት የርሃብ አደጋ ከተጋረጠባቸውና አስቸኳይ የሰብአዊ እርዳታ ከሚያስፈልጋቸው 17 ሚሊዮን ያህል ሰዎች መካከል 33 በመቶ ያህል የሚሆኑት ሶማሊያውያን መሆናቸውንና ከአገሪቱ ህዝብ ግማሽ ያህሉ የችግሩ ሰለባ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ባለፈው ማክሰኞ ሶማሊያን የጎበኙት ጉቴሬዝ፣ የዝናብ እጥረትና ግጭት በአገሪቱ የተከሰተውን ሰብአዊ ቀውስ እያባባሰው እንደሚገኝ በመጠቆም፤ አለማቀፉ ማህበረሰብ በሶማሊያና በሌሎች የምስራቅ አፍሪካ አገራት ለተከሰተው የርሃብ አደጋ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጥ ጠይቀዋል፡፡

ታዋቂው ድረገጽ ጎግል የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ስልጣናቸውን ያስረከቧቸውን አዲሱን ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕን ለማስገደል ሲያሴሩ ነበር በሚል ባለፈው እሁድ ያሰራጨው ሃሰተኛ መረጃ፣ ብዙዎችን እያነጋገረ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
በድረገጾች አማካይነት የሚሰራጩ ሃሰተኛ ዜናዎችን እየተከታተለ እንደሚያጠፋና አሳሳች መረጃዎችን እንደሚቃወም ከወራት በፊት በይፋ ያስታወቀው ጎግል፤ ፊቸርድ ስኒፔትስ በተባለው ልዩ የድረገጽ የመረጃ አገልግሎቱ ኦባማ ከቻይና ጋር በመተባበር ትራምፕን ለማስገደል ሲያሴሩ ነበር የሚል ሃሰተኛ መረጃ ማሰራጨቱን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ዌስተርን ሴንተር ፎር ጆርናሊዝም የተባለ ተቋም ይፋ ካደረገው ሚስጥራዊ ቪዲዮ አገኘሁት በሚል ጎግል ባለፈው እሁድ ይፋ ባደረገው በዚህ መረጃ፣ ኦባማ በስልጣን ዘመናቸው ማብቂያ ሰሞን ትራምፕን ለማስገደል ሲያሴሩ እንደነበር ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፣ ጉዳዩ ብዙዎችን ማነጋገር መጀመሩን ተከትሎ ጎግል መረጃው ሃሰተኛ ነው ሲል ማስተባበሉን ገልጧል፡፡
ጎግል ባወጣው የማስተባበያ መግለጫ ሆን ብሎ ሃሰተኛውን መረጃ እንዳላሰራጨ በመጥቀስ፣ ተጠቃሚዎች ለሚያነሷቸው የተለያዩ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥበት ፊቸርድ ስኒፔትስ የተባለው ልዩ የመረጃ አገልግሎቱ፣ ምላሾችን የሚሰጠው ከተለያዩ ድረገጾች የሚያገኛቸውን መረጃዎች መሰረት በማድረግ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ ያልተረጋገጠው መረጃ ከተጠቃሚዎች ዘንድ ሊደርስ መቻሉን አስታውቋል፡፡
ኦባማ በትራምፕ ላይ የግድያ ሴራ ሲያደርጉ ነበር የሚለው መረጃ ሃሰተኛ መሆኑን በማረጋገጥ በአፋጣኝ ከድረገጹ እንዲወገድ ማድረጉን የጠቆመው ጎግል፤ ሃሰተኛው መረጃ በመሰራጨቱ ሳቢያ ለሚደርሰው ማንኛውም ጉዳት ይቅርታ እንደሚጠይቅም ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡