Administrator

Administrator

  • 100 ሜትር በ56 ሰከንድ በክራንቾቹ ሮጧል፡፡
  • ሪከርዱ ገና በጊነስ መዝገብ እውቅና በማግኘት አልሰፈረም፡፡
  • የዩሲያን ቦልት አድናቂ ነው፡፡ ሊያገኘውም ይፈልጋል፡፡
  • በጀርመን ለመኖር የጥገኝነት ጥያቄ አቅርቧል፡፡
  • ከዓመት በፊት ስለህይወት ውጣውረዱና ሪከርድ ስለማስመዝገብ  አላማው ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረገው ቃለምልልስ ተናግሮ ነበር፡፡

   ከሳምንት በፊት “ፋርዝ” በተባለችና በሰሜን በቫርያ በምትገኝ የጀርመን ከተማ የ32 ዓመቱ ታምሩ ፀጋዬ በክራንቾቹ 100 ሜትርን በ56 ሴኮንዶች  በመሮጥ ባስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ አነጋጋሪ ሆኗል፡፡ ታዋቂው የእንግሊዝ ታብሎይድ ጋዜጣ ዴይልሜል በፃፈው ዘገባ  አካል ጉዳተኛው  ታምሩ ፀጋዬ በክራንቾቹ ተጠቅሞ 100 ሜትሩን በመሮጥ ያሳየው አስደናቂ ስፖርታዊ ብቃት ለመላው የሰው ልጆች ከፍተኛ የሞራል መነቃቃት የሚፈጥር ልዩ ስኬት ነው ብሎ አድንቆታል፡፡
የታምሩ ፀጋዬ  ልዩና አስገራሚ ሪከርድ በጊኒስ የሪከርዶች መዝገብ ገና አለመስፈሩን የዘገበው ጨምሮ የዘገበው ዴይሊ ሜል፤ በአጭር ጊዜ እውቅና ማግኘቱ እንደማይቀር ገልፆ፤ ሪከርዱን ያስመዘገበበት ትእይንት በአገሪቱ ብሄራዊ የቴሌቭዥን ጣቢያ ሽፋን ማግኘቱን አውስቷል፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኖ ለመንቀሳቀስ በሚጠቀምባቸው ክራንቾች አስገራሚና ልዩ ክብረወሰኖችን በማስመዝገብ የተሳካለትን እንግሊዛዊውን  ጆን ሳንድ ፎርድ የጠቀሰው የዴይሊ ሜል ዘገባ ታምሩ ለእነዚህ ክብረወሰኖች ተቀናቃኝ መሆን እንደሚችልም ጠቁሟል፡፡ እንግሊዛዊው አካል ጉዳተኛበክራንቾቹ በመታገዝ ሁለት የዓለም ክብረወሰኖችን በማሳካት በጊነስ የሪኮርዶች መዝገብ ሰፍሯል፡፡  ጆን ሳንድ ፎርድ  በ2009 እ.ኤ.አ ላይ የኪሊማንጀሮ ተራራን በ4 ቀናት ከ20 ሰዓታት እና ከ30 ደቂቃዎች የወጣ ሲሆን፤ በ2011 እ.ኤ.አ ላይ ደግሞ በለንደን ማራቶን በመሳተፍ 42.195 ኪ.ሜ ርቀትን በ6 ሰዓት ከ24 ደቂቃዎች ከ48 ሰኮንዶች ጨርሶ በእነዚህ ሁለት ልዩ ክብረወሰኖች በጊነስ የሪከርዶች መዝገብ ለመስፈር በቅቷል፡፡  ታምሩ ፀጋዬ በጀርመኗ ፋርዝ ከተማ ካስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ በኋላ  “አንድ በአንድ ህልሞቼን እያሳካሁ ነኝ፡፡ በህይወቴ ብዙ ውጣውረዶችን አሳልፌያለሁ፤ አካል ጉዳተኛ ብሆንም ብዙ ነገር ማድረግ እችላለሁ። በስፖርታዊ ብቃቴ እና አስደናቂ ተሰጥኦዎቼ ሌሎችን ሪኮርዶችን በማስመዝገብ መላው ዓለምን ማስደነቅ እፈልጋለሁ” ብሏል፡፡  ለዓለማችን ፈጣን የአጭር ርቀት ሯጭ ዮሴያን ቦልተ ከፍተኛ አድናቆት እንዳለው መናገሩን የጠቀሰው የዴይል ሜል ዘገባ “ዮሲያን ቦልትን እንደተምሳሌት የምመለከተው ጀግና ነው፡፡ እኔም ምርጥ ስፖርተኛ ነኝ፡፡ እሱ በፈጣን እግሮቹ እንደተሳካለት በጠንካራ እጆቼ በክራንቾቼ በመሮጥ ሪከርድ አስመዝግቢያለሁ፡፡ የሰራሁትን ታሪክ ቢያይልኝና ባገኘውገኘውም ደስ ይለኛል” ብሎ መናገሩንም አውስቷል፡፡
በሌላ በኩል ታምሩ ፀጋዬ ባለፉት ጥቂት ወራት በመላው አውሮፓ ከሚታወቀው እና “ሲርኪዊ ዲ ሶሊል” ከተባለ የሰርከስ ቡድን ጋር  እየሰራ እንደሚገኝ ያመለከተው አንድ የጀርመን ሚዲያ፤ በተለያዩ የጀርመን ከተሞች በመዘዋወር ትርኢቶችን ማቅረቡን  እንደሚቀጥል ቢገልፅም ወደ አገሩ ለመመለስ ፍላጐት እንደሌለውና በጀርመን አገር ለመኖር የጥገኝነት ማመልከቻ ማስገባቱን ጎን ለጎን ዘግቧል፡፡
በአዲስ አድማስ ያደረገው ቃለምልልስ
ታምሩ ፀጋዬ ለአስራ አምስት ዓመት እግሮቹ መራመድ ስለማይችሉ እጁን እንደ እግር በመጠቀም እየተሳበ ነበር የሚጓዘው፡፡ እናትና አባቱ አግልለውታል፡፡ ከቤተሰብ፣ ከማህበረሰብና ከጓደኞች ብዙ ተፅዕኖ፣ ብዙ ንቀትና ጥላቻ ደርሶበታል፡፡ ማደርያ አጥቶ ጐዳና አድሯል፤ ሊስትሮነትም ሰርቷል፡፡ ግን ሁሌም ትልቅ ታሪክ የመስራት ሪከርድ የማስመዝገብ ህልም እንደነበረው ከዓመት በፊት የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ከሆነችው አበባየሁ ገበያው ጋር ባደረገው ቃለምምልስ ተናግሮ ነበር፡፡  ታምሩ በክራንች በመታገዝ መንቀሳቀስ የቻለበትን ከፍተኛ የቀዶ ጥገና ህክምና ያገኘው በአጋጣሚ ነው፡፡ “ተዓምር” ከሚመስል ህክምናው በኋላ በእግሩ መሄድ ጀመረና በ16 ዓመቱ አንደኛ ክፍል ገባ፡፡ እስከ ኮሌጅ ዘለቀ፡፡ ከዛም ወደ ስፖርት ገባ፡፡ ሪከርድ ለማስመዝገብ አለመ፡፡ ይህንንም ፊልም የሚመስለው አስገራሚ የህይወት ታሪኩን በወቅቱ ከጋዜጣው ጋር ባደረገው ቃለምልልስ በስፋት ሲያወጋ ሁሉንም የህይወት ተሞክሮውን በማጠቃለል ሲናገር ወደቅሁ፤ ተጋጋጥኩ፤ ግን ተሳካልኝ  ብሎ ነበር፡፡ ታምሩ ፀጋዬ ከሳምንት በፊት ካስመዘገበው ልዩ የዓለም ሪከርድ በኋላ ከዓመት በፊት ከአዲስ አድማስ ጋር ካደረገው ቃለምልልስ አንዳንድ ምላሾቹን ለትውስታ እንዲህ ይቀርባሉ፡፡
‹‹ስወለድ አፈጣጠሬ የሚያስደንቅ ስለነበረ ፈቃዱ ዘገዬ አሉኝ፡፡ “እሱ እንደፈቀደ፣ እንደፈጠረው የሚያደርገውን ያድርገው” ለማለት ይመስለኛል፡፡ ታምሩ የሚለው ግን የቆሎ ት/ቤት እያለሁ የወጣልኝ ስም ነው፡፡ ይሄም ተመሳሳይ ትርጉም አለው፡፡ ሁለቱም እግሮቼ ስወለድ ወደ ኋላ ተቆልምመው ነው የተወለድኩት፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኜ ማለት ነው፤… የተወለድኩት ከላሊበላ 60 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ባለች የገጠር ሰፈር (ምዢ ማርያም በምትባል ቦታ) ነው፡፡ እናቴ፤ አያቴ ቤት  በቤት ሠራተኝነት ታገለግል ነበር፡፡ እኔ የተረገዝኩት አባቴ ከእናቴ ጋር በነበረው የምስጢር ግንኙነት ነው፡፡ አባቴ ሊዳር ሁለት ወር ሲቀረው እኔ ተወለድኩ፡፡›› በማለት ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ የልጅነት ታሪኩን አጫውቷል፡፡
ስትወለድ በቤት ውስጥ የነበረው ስሜት እንዴት ነበር፤ ካደግህ በኋላ ስትሰማ ምን ስሜት ተፈጠረብህ በሚል ጥያቄ ቀርቦለት ነበር፡፡ ታምሩ ፀጋዬ ምላሹን ሲሰጥ‹‹ ለእናቴም ለእኔም መጥፎ እንደነበር ዛሬ ዛሬ እሰማለሁ፡፡ አካል ጉዳተኛ ሆኜ በመወለዴ የአባቴ ቤተሰቦች ‹‹ይሄ ልጅ ከእኛ ዘር አይደለም፤ ዘር አሰዳቢ ነው›› ይሉ ነበር፡፡ እናቴ መረራትና ጥላኝ ጠፋች፡፡  ለ3 ወር ብቻ ጡት አጥብታኝና ከተማ ገባች፡፡ ሴት አያቴ ደረቅ ጡቷን ታጠባኝ ነበር፡፡ እናቴ  ካደግሁ በኋላ አልፎ አልፎ ቤተሰብ ለመጠየቅ ትመጣ ነበር፡፡ እኔን ያሳደገኝ አያቴ ነው፡፡ እስከ አምስት አመቴ ድረስ ከቤት መውጣት አልችልም ነበር፡፡ አፈና ተደርጐብኝ ሳይሆን በቃ መራመድ አልችልም፡፡ እንደ እባብ ነበር የምሳበው፤ በእጄ እየተራመድኩ፣ እጄን እንደ እግር እየተጠቀምኩ ማለት ነው፡፡ ሰው ስለሚያገለኝ ብቻዬን አወራለሁ፤ ብቻዬን እጫወታለሁ፡፡ አያቴ ቄስ ትምህርት ቤት እንድማር ይፈልግ ነበር…ያኔ በየደብሩ ቄስ ትምህርት ቤት አለ፡፡ እኔ ግን ፍላጐቴ ጨዋታ ብቻ ነው፡፡ በእጄ እየተሳብኩ …በሩጫም እንኳን የሚቀድመኝ አልነበረም፡፡ አያቴ የትምህርት ፍላጐት እንደሌለኝ ሲረዳ ከብት ጠባቂ አደረገኝ፡፡›› በማለት ያሳለፈውን የህይወት ውጣውረድ ገልፆታል፡፡
እንዴት የስፖርት እንቅስቃሴዎችን ማድረግ እንደጀመረ ሲናገር ደግሞ ‹‹ብቻዬን፡፡ አንድ ጓደኛዬ ነበር፤ ያየኛል፤ አብሮኝም ይሰራል፡፡ የማልሞክረው ነገር የለም፡፡ ኦፕራሲዮን አድርጌ በክራንች ነበር የምሄደው፡፡ ስለዚህ ለምን ተዘቅዝቄ በክራንች በእጄ አልሄድም ብዬ ተነሳሁ፡፡ በኢንተርኔት ላይ እንደዚህ ዓይነት ሪከርድ ያስመዘገበ የለም፡፡ በዚህ መንገድ ለምን ራሴን አላወጣም ብዬ ጀመርኩ። ወደቅሁ፣ ተነሳሁ፣ ተጋጋጥኩ፡፡ አሁን ከመቶ ሜትር በላይ እሄዳለሁ፡፡ የሚፈለገው በአንድ ደቂቃ ውስጥ ምን ያህል ሜትር ይኬዳል የሚለው ነገር ነው።›› ብሎም ነበር፡፡  በዓለም ላይ እንደዚህ ዓይነት ጅምናስቲክ የሚሰራ እንዳለም ተጠይቆ ነበር፡፡ ‹‹የለም፡፡ ተዘቅዝቆ በክራንች ላይ በእጅ በመሄድ እኔ ብቻ ነኝ፡፡ ቆየሁና ለምን በክራንች ላይ ሆኜ ደረጃ አልወርድም አልኩና ልምምድ ጀመርኩ፡፡ በተደጋጋሚ ወደቅሁ፤ ተጋጋጥኩ ግን አደረግሁት።›› የሚል ምላሽ ሰጥቶ የነበረው ታምሩ ፀጋዬ በዚያው ቃለምልልስ ለማስመዝገብ ስላሰበው ሪኮርዱ ስኬታማነት ማብራርያ እንዲሰጥ ተደርጎም ነበር፡፡ ‹‹በአንድ ደቂቃ ከ76 ሜትር በላይ ተዘቅዝቆ በክራንች ላይ በእጅ በመሄድ ሶስት ድርጅቶች እውቅና ሰጥተውኛል፡፡ “ወርልድ ሪኮርድ አካዳሚ”፣ “ወርልድ ሪኮርድ ሴንተር”፣ እና “ወርልድ ኦቶራይዝ›› ናቸው፡፡ የእነዚህ ሪከርዶች ባለቤት ነኝ፡፡ ሁለቱ ሪከርዶች ያገኘሁት በክራንች በመሄድ ነው፡፡ የራሴን ስም አስጠርቼ አገሬን ማስጠራት ነበር የምፈልገው፡፡ ይሄው ተሳካልኝ፡፡ ጊነስ ወርልድ ሪከርድ በዚህ ወር እውቅና ይሰጠኛል፡፡›› ብሎ ነበር፡፡  

         በአንድ እጇ አሜሪካ ውስጥ በሌላው እጇ አፍሪካ ውስጥ ስኬታማ ሥራ ፈጣሪ የቢዝነስ ባለሙያ የሆነችው ሶፊያ በቀለ እሸቴ፣ ወንዶች በገነኑበት የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ፣ በኩባንያ አስተዳደር፣ እንዲሁም በስጋት አያያዝና አወጋገድ ዙሪያ አንቱ የተሰኘች ባለሙያ ነች። በመረጃ (በኢንፎርሜሽን) ደህንነት፣ ጥበቃና ምርመራ ዙሪያ በአለማቀፍ የአሜሪካ ኩባንያዎች ውስጥ ለበርካታ አመታት የሰራችው ሶፊያ፤ እጇን ወደ አፍሪካ በመዘርጋት እንደ አገር ግንባታ ሊቆጠሩ የሚችሉ ግዙፍ ፕሮጀክቶችን አከናውናለች። ለአፍሪካ ህብረት እና ለኢትዮጵያ ፓርላማ የተቀናጀ የመረጃ አያያዝና አጠቃቀም ስርዓቶችን ዘርግታለች።
ከዚያም የኢንተርኔት ግንኙነትን ከአደጋ ለመጠበቅ በሚያስፈልጉ ጥንቃቄዎችና እርምጃዎች ዙሪያ የኩባንያ አስተዳደርና የስጋት አያያዝ አማካሪ ሆና ሰርታለች። የኩባንያ ግንባታና የኮሙኒኬሽን አማካሪ በመሆን የአሜሪካ ኩባንያዎችን ከማገልገሏ በተጨማሪ፣ በአለማቀፍ ደረጃም የኢንተርኔት ፖሊሲ አማካሪ ሆናለች። በቅርቡ ደግሞ፣ ዶትኮኔክት አፍሪካ ትረስት (ባለአደራ) እንዲሁም ዶትኮኔክትአፍሪካ ረጂስትሪ ሰርቪስስ ሊሚትድ የተሰኙ ተቋማትን መስርታለች። በዚህም በመላው አለም የሚኖሩ አፍሪካዊያንን በመወከል .africa የተሰኘ የኢንተርኔት አድራሻ ስርወ-ስያሜ ለመፍጠርና በበላይነት ለማስተዳደር ጥያቄ አቅርባለች።  በሰኔ 2004 ዓ.ም ማመልከቻ ያስገባችው፤ አሜሪካ ለሚገኘውና የኢንተርኔት አድራሻዎችን ለሚያስተዳድረው አትራፊ ያልሆነ አለማቀፍ ድርጅት ICANN ነው። ድርጅቱ ውስጥ በምክር ቤት አባልነት ትሰራ በነበረበት ወቅት ነው የዶትአፍሪካ ፕሮጀክቷን የጀመረችው። ዶትኮኔክትአፍሪካ የተሰኙ ተቋሞቿ፤ ለፕሮጀክቱ ስኬታማነት የሚያደርጉት አስተዋፅኦ ቀላል አይደለም። ተቋሞቿ Yes2dotAfrica  በሚል መሪ ቃል ለስድስት አመታት ያካሄዱት አለማቀፍ የግንዛቤ ማስፋፊያ ዘመቻ ተቀባይነትን አስገኝቶላቸዋል። ዘመቻው፤ በአፍሪካ ስም የኢንተርኔት አድራሻ የመፍጠር ጉዳይ ብቻ አይደለም። በመላው አለም የአፍሪካን መልካም ገፅታ ለመገንባት ልዩ እድል ይሰጣል። በዚያ ላይ፤ የአፍሪካ ሴቶችንና ወጣቶችን፣ በኢንተርኔት አብዮት ውስጥ በዋና ተዋናይነት የሚያሳትፉ በርካታ ፕሮጀክቶችንና እቅዶችን ለማፍለቅ ጥሩ መነሻ ይሆናል።
በአዲስ አበባ የተወለደችው ሶፊያ፣ በወላጆቿ የተደላደለ ኑሮና በጥሩ ትምህርት ነው ያደገችው። ኢትዮጵያ ውስት በተለያዩ የቢዝነስ መስኮች ስኬታማ በመሆን የሚታወቁት አባቷ አቶ በቀለ እሸቴ፤ የህብረት ባንክ እና የህብረት ኢንሹራንስ መስራችና የቦርድ አባል ነበሩ። በአገሪቱ በትልቅነታቸው ከሚታወቁ የገንዘብ ተቋማት መካከልት ህብረት ባንክና ኢንሹራንስ ተጠቃሽ ናቸው። ሶፊያ ከቢዝነሱ ዓለም ጋር የተዋወቀችው፣ ከአባቷ አፍ ነው። ስለ ራሳቸው ስራ ከጓደኞችና ከቤተሰብ አባላት ጋር ሲያወሩ እየሰማች፣ የቢዝነስን አሰራር ትምህርት ቀስማለች። ራስን ችሎ የመወሰንና የመኖር ጥቅምን ከአባቷ የተማረችው ሶፊያ፤ ከስጋት የፀዳ የቢዝነስ ሥራ እንደሌለና ከበርካታ ስጋት አዘል የቢዝነስ አማራጮች መካከል የተሻለውን መርጦ የመግባት ድፍረት አስፈላጊ እንደሆነም መሰረታዊ እውቀት አስጨብጠዋታል።
እናቷ ሲስተር ሙሉዓለም በየነ፣ በሙያቸው ለበርካታ ዓመታት የሰሩ ነርስ ሲሆኑ፣ የማምለክ ያህል በፍቅር ታከብራቸዋለች። ርህራሄንና ደግነትን የተላበሱ በጣም ሃይማኖተኛ ሴት ነበሩ።  በተደላደለ ኑሮ ውስጥ ምንም ሳይጎድልባት ያደገችው ሶፊያ፤ ጥራት ያለው ትምህርት በማግኘትም እድለኛ ነች። ከታላቅ እህቷ ጋር የመጀመሪያና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን የተከታተለችው በአዲስ አበባ ናዝሬት ስኩል ነው። የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቷን እንዳጠናቀቀች፣ ከታላቅ እህቷ ጋር አሜሪካ ሄደው ዩኒቨርስቲ እንዲገቡ ስፖንሰር ስለተገኘላቸው፤ ወደ ሳን ፍራንሲስኮ ካሊፎርኒያ በረረች። በእርግጥ የዩኒቨርሲቲ ወጪያቸውን የሸፈኑት ወላጆቻቸው ናቸው። ከአሜሪካ ኑሮ ጋር መላመድ ለእህትማማቾቹ ፈተና እንደነበር ሶፊያ ስታስታውስ፤ ከተማ ውስጥ ወዲህ ወዲያ ለማለት እንኳ እንደተቸገሩ ትናገራለች። ወቅት የሚከተል የአሜሪካ ዘመነኛ ባህልን በቅጡ ለመገንዘብና መውጪያ መግቢያውን ለማወቅ ጊዜ የፈጀባቸው ሶፊያና እህቷ፤ የራሳቸውን ባህል እንደያዙ የአሜሪካዊያን ሕይወት ውስጥ መቀላቀል ቀላል አልሆነላቸውም። ደግነቱ፤  ጥራት ባለው የናዝሬት ስኩል ትምህርት የታነፁት እህትማማቾች፣ በሳን ፍራንሲስኮ ስቴት ዩኒቨርስቲ ውስጥ ከሌሎች ተማሪዎች ልቀው ለመገኘት አልተቸገሩም። ለነገሩማ ለተወሰነ ጊዜ ቢደነጋገርባቸውም ከአሜሪካ ኑሮ ጋር መቀላቀላቸው አልቀረም። ከጊዜ በኋላማ ሶፊያ የአሜሪካን ሕይወት መውደድ ጀመረች። ለካ አሜሪካ ልዩ ፀጋ አላት። የአገሪቱ የነፃነት መንፈስ ግሩም ነው፤ ሕይወትን ለማሻሻልና ለመሥራት  ሰፊ እድል የሚገኝባት አገር መሆኗም ድንቅ ነው። ባየችውና ባስተዋለችው መልካም ህይወት ለአሜሪካ ፍቅር ያደረባት ሶፊያ፤ ወደፊትም ያንን አገር ሳትለቅ ነው አፍሪካ ውስጥ እግሯን መትከል የምትሻው። በቢዝነስ አናሊሲስና በመረጃ ሥርዓት (በኢንፎርሜሽን ሲስተምስ) የመጀመሪያ ዲግሪዋን ከያዘች በኋላ፤ በጎልደን ጌት ዩኒቨርስቲ በማኔጅመንት የመረጃ ሥርዓት ማስተርስ ዲግሪ አግኝታለች። ሥራ ፍለጋ ላይ ታች አላለችም። ሥራው ራሱ ነው እሷን ፍለጋ ዩኒቨርሲቲው ድረስ የመጣላት። በዩኒቨርስቲ እጅግ የላቀ ውጤት የሚያስመዘግቡ ተመራቂዎች፣ ከዩኒቨርሲቲው ሳይወጡ ነው በተለያዩ ምርጥ ኩባንያዎች ተመልምለው ሥራ የሚቀጠሩት። ሶፊያም በወቅቱ በግዙፍነታቸው ከሚታወቁ ባንኮች መካከል አንዱ በሆነው ባንክ ኦፍ አሜሪካ ለኮምፒዩተር ኦዲቲንግ ሥራ ተቀጠረች። በእርግጥ በቀጥታ ሥራ አልጀመረችም። የመረጃ ሥርዓት ደህንነትና ቅልጥፍና፣ በተለይ ደግሞ የመረጃ አጠቃቀምና ጥበቃ ላይ ያተኮረው የኮምፒዩተር ኦዲቲንግ ሥራ፣ ልዩ እውቀት የሚያስፈልገው በጣም አዲስ የሙያ መስክ ስለነበረ፤ ሶፊያና አብረዋት የተቀጠሩ ባልደረቦቿ ባንክ አሜሪካ ውስጥ ተጨማሪ ስልጠና ተሰጥቷቸዋል። እዚህ ወንዶች የገነኑበት ሙያ ውስጥ ነው፤ ሶፊያ ስለ ወንዶች ብዙ ማወቅ የጀመረችው። ወንዶች በበዙበት ድባብ ውስጥ እንዴት ስኬታማና ውጤታማ መሆን እንደምትችል ትምህርት የቀሰመችውም፤ በዚሁ ሥራዋ ነው። ዩኒየንባንካል ወደ ተሰኘው ኮርፖሬሽን ከተሻገረች በኋላ፣ ወደ ሥራ አስኪያጅ የሃላፊነት ደረጃ እድገት አግኝታ ሠርታለች። ከዚያም በአለም በትልቅነታቸው ከሚታወቁ የአካውንቲንግ አገልግሎትና የኢንቨስትመንት አማካሪ ድርጅቶች መካከል አንዱ በሆነው ኩባንያ ተቀጠረች - በፕራይስ ወተርሃውስ ኩፐርስ። ኢንሹራንስና ባንክ የመሳሰሉ ድርጅቶች ገንዘብ ወይም የዋስትና ሰነድ ታቅፈው አይቀመጡም፤ በትርፋማ ነገር ላይ ሊያውሉት ይሞክራሉ እንጂ። ግን ደግሞ፤ ገንዘብ ሲፈልጉ ወዲያውኑ መልሰው ሊያገኙት ይገባል። መፍትሄው፤ ከበርካታ ኩባንያዎችና ተቋማት አክሲዮን ወይም ቦንድ መግዛት ነው። ገንዘባቸውን ትርፋማ ያደርግላቸዋል፤ በአፋጣኝ ገንዘብ ካስፈለጋቸውም የገዙትን አክስዮንና ቦንድ መሸጥ ይችላሉ። እንዲህ በአክስዮንና  በቦንድ ግብይት ገንዘብን ውጤታማ የማድረግ አሰራር፣ ፓርትፎሊዮ ኢንቨስትመንት ይሉታል። ነገር ግን እጅግ አዋቂነትንና ብልህነትን ስለሚጠይቅ፤ በባለሙያ አማካሪዎች አማካኝነት መመራት ይኖርበታል። ፕራይስ ወተርሃውስ ኩፐርስ በተሰኘው ኩባንያ ውስጥ የሶፊያ ዋና ሥራም፣ ለተለያዩ ደንበኞች የፖርትፎሊዮ ኢንቨስትመንት አማካሪ ሆና በበላይነት መቆጣጠር ነበር። የሶፊያን ምክር ከሚቀበሉ ደንበኞች መካከልም በእንግሊዝ ከአራቱ ትልልቅ ባንኮች መካከል አንዱ የሆነው በርክለይ ባንክ ይገኝበታል። ከጤና አገልግሎት ኢንሹራንስ ጋር ለተያያዙና ለሌሎች ኩባንያዎችም የአማካሪነትን ስራ በበላይነት መርታለች። እዚህ ነው ሥራ መምራትን የተካነችው። በአይነትና በመጠን ከሚለያዩ በርካታ ባለሙያዎችና ቡድኖች ጋር የመስራት ችሎታዋ፣ ውስብስብና ግዙፍ ፕሮጀክቶችን የመምራት ጥበቧና ብቃቷ ወደ ላቀ ደረጃ ተሸጋገረ። ይሄኔ ነው የራሷን ድርጅት ለመክፈት የሚያስችል ክህሎትና በራስ የመተማመን መንፈስ መጎናፀፏን እርግጠኛ የሆነችው።
ኩባንያውን ከለቀቀች በኋላ፣ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች ስትዟዟር አንድ አመት አሳለፈች። የሥራ ፈት ዙረት አይደለም። ከአሜሪካ አውሮፓ፣ ከኤስያ ላቲን አሜሪካ ድረስ ወደ ተለያዩ አገራት የተጓዘችው፣ በየአገሩ ያለውን የቢዝነስ አሰራርና ባህል እንዲሁም፤ የኢንተርኔትና የቴክኖሎጂ ደረጃ ለመመልከት ነው። አሜሪካ ውስጥ ሆና በየአህጉሩ ገና በመመንደግ ላይ ለሚገኙ አገራት የቴክኖሎጂ ሽግግር የማካሄድ አላማና የቢዝነስ ውጥን የያዘችው ሶፊያ፣  በ1990 ዓ.ም ሲቢኤስ ኢንተርናሽናል በሚል ስያሜ የራሷን ኩባንያ መሰረተች። በተመሳሳይ አላማም ኢትዮጵያ ውስጥ በ”ሲስተም ኢንተግሬሽን” ሥራዎች ላይ ያተኮረ “ኤስቢኮሙኒኬሽንስ ኔትዎርክ” የተሰኘ ኩባንያ አቋቋመች። ለአፍሪካ ህብረት የቴክኖሎጂ መሰረተ ልማት ለመዘርጋት በጨረታ ተወዳድራ ያሸነፈችው ሶፊያ፣ ለጨረታው የመረጠችው የቢዝነስ ዘዴ፣ በኢትዮጵያ ያን ያህልም የተለመደ አልነበረም። የፕሮጀክት አመራር ላይ በተመሰረተ የቢዝነስ ዘዴ ከአገር ውስጥና ከውጭ ባለሙያዎችንና የተለያዩ ድርጅቶችን አሰባስባ በማስተባበር ጨረታውን ካሸነፈች በኋላ፤ ስራውንም በተመሳሳይ መንገድ አጠናቅቃ ለአገልግሎት አብቅታለች። ገና የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ባላደገበት አገር፣ በግዙፍነቱ ተጠቃሽ የሆነ የአፍሪካ ህብረት ፕሮጀክት ላይ ውጤታማነቷን ያስመሰከረችው ሶፊያ፤ ወደ ሌላ ትልቅ ፕሮጀክት አመራች። ለኢትዮጵያ ፓርላማ የመረጃ አያያዝና አጠቃቀም ስርዓት ለመዘርጋት፤ እንደገና ዳይሜንሽን ዳታ የተባለ የደቡብ አፍሪካ ኩባንያን ጨምሮ ከተለያዩ አገራት የተውጣጣ ቡድን በመፍጠር ጨረታ አሸንፋ ፕሮጀክቱን በስኬት ፈፅማለች። ከፕሮጀክቱ ጋር ተያይዞ በተፈጠረ ውዝግብ የተነሳ በአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን በሰፊ መዘገቡ የሚታወስ ሲሆን፣ የውዝግቡ መነሻ አድሎአዊ አሰራርን በመቃወም ሶፊያ ያቀረበችው ጥያቄ ነው። የግዢና የኮንትራት ሥርዓቱ ላይ ፍትሃዊነት የጎደለው አሰራር መኖሩን በመቃወም ተከራክራ ለማሸነፍ የበቃችው ሶፊያ፤ የመንግስት የግዢና የኮንትራት አሰራር እንዲሻሻል፣ ግልፅነትና ተጠያቂነትንም እንዲላበስ ክርክሯ አስተዋፅኦ እንዳደረገ ታምናለች። በ1994 ዓ.ም በግሉ ዘርፍ የተቋቋመ ቡድን ኢትዮጵያ ውስጥ የአክሲዮን ገበያ ለመመስረት በማቀድ ለመንግስት ያቀረበው ሃሳብ ስህተቶችና ጉድለቶች እንደነበሩት የምትገልፀው ሶፊያ፣ በመርህ ላይ የተመሰረተ ተቃውሞ እንዳስተጋባች ታስታውሳለች። በዚያው አመት መጨረሻ ላይም ለአክሲዮን ገበያ የቀረበው ሃሳብ በመንግስት ውድቅ ተደርጓል። ምናልባትም በወቅቱ ባስተጋባችው አቋም፣ የኋላ ኋላ የኢትዮጵያ እህል ገበያ እንዲመሰረት መንገዱን የሚጠርግ ነበር ብላ ታስባለች። ኢትዮጵያ ውስጥ አዘውትራ የሰራችበት ያንን ጊዜ ትወደዋለች። ከዘመድ አዝማድም ጋር ጥሩ ጊዜ ለማሳለፍ አስችሏት ነበር። በእርግጥ እያሰለሰች ወደ አሜሪካ መመላለሷ አልቀረም። ኩባንያ ወደሚገኝበት ወደ ካሊፎርኒያ እንዲሁም የቴክኖሎጂ ቁሳቁስ አቅራቢዎቿ ወደሚገኙበት ሚያሚ በተደጋጋሚ ተመላልሳለች። እዚህ ኢትዮጵያ ውስጥ ለአገሯ ተጨባጭ አስተዋፅኦ የሚያበረክት ፕሮጀክት ያከናወነችበት ወቅት ስለሆነ ግን ያንን ጊዜ ትወደዋለች።
ኢትዮጵያ ውስጥ የጀመረችውን የፓርላማ ፕሮጀክት እንዳጠናቀቀች፣ ብዙም ሳይቆይ አሜሪካ ውስጥ ሌላ የቢዝነስ እድል ታያት። በአሜሪካ በግዙፍነቱ 7ኛ ደረጃ ላይ የነበረው ኢንሮን ኩባንያ እንዲሁም በቴሌኮሙኒኬሽንና በኢንተርኔት ቢዝነስ በትልቅነቱ የሚታወቀው ዎርልድኮም ኩባንያ በኪሳራ መዘፈቃቸው በድንገት ይፋ የወጣበትና የዓለም መነጋገሪያ የሆኑበት ወቅት ነበር - ጊዜው።  በእርግጥ ኩባንያዎቹ በድንገት አልከሰሩም። ቅጥ ባጣ የኩባንያ አመራርና በአሳሳች የመረጃ አቀራረብ ለበርካታ አመታት ኪሳራቸው እንዲደበቅ ተደርጓል። የተደበቁት ጉዶች ሲያብጡ ከርመው ድንገት ሲፈነዱ፤ በቢዝነስ ዓለም ከታዩት ትልልቅ ቅሌቶች ተርታ የሚመደቡ ሆነው አረፉት። ታዲያ ለእንዲህ አይነት የመረጃ አጠቃቀምና የኩባንያ አመራር ችግሮች መፍትሄያቸው ምንድነው? ችግሮች ሲኖሩ፣ መፍትሄ ይዞ የሚመጣ ሰው የቢዝነስ እድል ያገኛል።  ሶፊያም በዚህ ምክንያት ነው የቢዝነስ እድል የታያት። የመረጃ ስርዓት ቅልጥፍናንና አጠቃቀምን የመመርመር ሙያዋ ይታወቃል። በትልልቅ ኩባንያዎች ውስጥ በሥራ አመራር የሃላፊነት ደረጃ ሠርታለች። የኩባንያ ንብረቶችን በአግባቡ ለማስተዳደርና ለመምራት፤ የመረጃ ሥርዓት የቱን ያህል ቁልፍ እንደሆነ ታውቃለች። በዚህ ዙሪያ በአማካሪነት ለመስራት በከፈተችው የቢዝነስ ሥራ፣ ካሊፎርኒያ ውስጥ ለሚገኙ በርካታ የሲልከን ቫሊ ኩባንያዎች የምክር አገልግሎት ሰጥታለች - ለኢንተል፣ ጀኔነቴክ፣ ኦንስክሪን ወዘተ።  ለአገሪቱ ብሄራዊ ባንክ (ፌደራል ሪዘርቭ ባንክ) እንዲሁም ለሌሎች ተቋማትም አገልግሎቷን በማስፋፋት ስኬታማ ቢዝነስ ገንብታለች። በኩባንያ ግንባታና በኮሙኒኬሽን እቅዶች ላይም ለበርካታ የአሜሪካ ኩባንያዎች በአማካሪነት የሰራችው ሶፊያ፣ የሥራ ፈጠራ ኢንቨስትመንት (ቬንቸር ካፒታል)፣ የኮንትራት ሃላፊነትና አፈፃፀም፣ የገበያ እድል ማመቻቸትና ማስፋት፣ የገበያ ድርድር፣ የቢዝነስ እቅድ አመዛዘንና አፈታተሽ፣ የዓለማቀፍ  ትስስር ስትራቴጂያዊ እቅድ አዘገዳጃጀት፣ የሕዝብ ግንኙነት ስትራቴጂ አዘገጃጀትና አፈፃፀም፣ እንዲሁም በሌሎች ጉዳዮች ላይ የአማካሪነት አገልግሎት አስፋፍታለች።
አዲሱ የአማካሪነት ቢዝነሷን እያስፋፋች ሳለ ነው ተጨማሪ የሥራ አቅጣጫ የሚፈጥርላት አጋጣሚ የተፈጠረው። የኢንተርኔት አድራሻዎችን በሃላፊነት ለማስተዳደር፣ በዓለማቀፍ ደረጃ በመንግስታዊና በግል ዘርፍ ተቋማት ትብብር የተመሰረተው ድርጅት (ICANN)  ውስጥ የምክር ቤት አባል እንድትሆን ተመረጠች። ምክር ቤቱ አንዱ ትኩረት የኢንተርኔት አድራሻ ስርወ-ስያሜ ነው። ለምሳሌ .com, .edu, .gov, .net, .org... የመሳሰሉ አዳዲስ ስርወ-ስያሜዎች ስራ ላይ የሚውሉት በምክር ቤቱ ከታዩና ውይይት ከተካሄደባቸው በኋላ ነው። በስርወ ስያሜዎች አጠቃቀም ላይ በአማካሪነት እንድትሰራ ሃላፊነት የተሰጣት ሶፊያ፣ የኢንተርኔት አድራሻ አሰያየም ላይ መላው የዓለም ማህበረሰብ የመሳተፍ እድል እንዲያገኝ የሚያግዝ የፖሊሲ መመሪያ በማርቀቅ አቅርባለች። ላበረከተችው አስተዋፅኦም በዓለማቀፍ ደረጃ እውቅና ተሰጥቷታል - Internationalized Domain Resolution Union (IDRU) በተሰኘ ቡድን። ሶፊያ የኢንተርኔት አድራሻዎች ላይ በአማካሪነት በምትሰራበት ወቅት ነው፣ ለአፍሪካ ልዩ ትርጉም የያዘ ሃሳብ የመጣላት። .africa የተሰኘ የኢንተርኔት አድራሻ ስርወ-ስያሜ መፍጠርና ሥራ ላይ ማዋል እንደሚቻል በመገንዘብም፣  በ1998 ዓ.ም ዶትኮኔክትአፍሪካ የተሰኘ እቅዷን ማስተዋወቅ ጀመረች። እቅዷም፣ በተለይም በተመድ የአፍሪካ ኢኮኖሚክ ኮሚሽን፣ እንዲሁም በአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ፈጣን ድጋፍ አግኝቷል። የመሪነቱን ሃላፊነት በመውሰድ ከተለያዩ አገራት የተውጣጡ ባለሙያዎችን አሰባስባ ማመልከቻ በማዘጋጀት፣ በ2004 ዓ.ም ጥያቄዋን ICANN አስገብታለች። .africa የሚል የኢንተርኔት ስርወ-ሥያሜ ሥራ ላይ እንዲውል የቀረበው ማመልከቻ ላይ  በ2005 ዓ.ም የመጀመሪያዎቹ ወራት ላይ ውሳኔ ይሰጥበታል ተብሎ ይጠበቃል። ሶፊያና ባልደረቦቿ አወንታዊ ምላሽ ያግኙ እንጂ፣ የአፍሪካን መልካም ገፅታ በሚገነባ መንገድ ስርወ-ሥያሜውን ለማስጀመር ዝግጁ ነች። ከዚህም ጋር በማያያዝ፤ የአፍሪካ ሴቶችና ወጣቶች በቴክኖሎጂ መስክ ብቃትና አቅም የሚያዳብሩበት፣ እንዲሁም ቢዝነሳቸውን በቴክኖሎጂ የሚያጎለብቱበት ብዙ አይነት እቅዶችን ተግባራዊ ማድረግ ይቻላል እያለች በጉጉት ታስባለች። የተራቀቀ የኢንተርኔት አገልግሎቶችን ጨምሮ ዘመናዊ የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂን የመሰለ ሃያል መሳሪያ ወደ ታዳጊ አገራት ለማሸጋገር ባከናወነችው ሥራ ላይ ገለፃ እንድትሰጥ በተደጋጋሚ እየተጋበዘች ተመክሮዋን በተለያዩ መድረኮች አካፍላለች። በኒውዮርክ በተካሄደ የተባበሩት መንግስትት ጠቅላላ ጉባኤ፣ ሩዋንዳ ኪጋሊ በተካሄደ የአፍሪካ መሪዎች የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ስብሰባ፣ እንዲህም በካሊፎርኒያ የስታንፎርድ ሴት የቢዝነስ ባለሙያዎች ስብሰባ ላይ ተሞክሮዋን አቅርባለች።
ሶፊያ ከሙያ ሕይወቷ በተጨማሪ በማህበራዊ አገልግሎቶች ውስጥም ለመሳተፍ ጊዜ አላጣችም። በሮታሪ ክለብ፣ በመረጃ ሥርዓት ኦዲትና ቁጥጥር ማህበር፣ በጎልደን ጌት ዩኒቨርሲቲ ተመራቂዎች ማህበር የዳሬክተሮች ቦርድ ውስጥ የምትሳተፈው ሶፊያ፣ የሳን ፍራንሲስኮ ቤይ የኢንተርኔት ማህበረሰብን ከመሰረቱት ሰዎች አንዷ ከመሆኗም በላይ የሥራ አስፈፃሚ ቦርድ አባል ናት።
በአብዛኛው ወንዶች በገነኑበት የሙያ ዘርፍ ውስጥ በመስራት ካስተዋለችው ተነስታ ስትናገር፣ ሴቶች ተቀባይነት ለማግኘት በላቀ ብልሃትና ትጋት መስራት ይጠበቅባቸዋል ትላለች። ዋናው ነገር፣ በቁርጠኝነት የሙጢኝ ብሎ መሥራት ነው። ከዚህም በተጨማሪ ሥራዎችሽ እንዲታወቁና እንዲታዩ ማድረግ ያስፈልጋል። ስራዎችሽ ተደብቀው ከቀሩ፣ መልካም ስምንና ዝናን መገንባት አትችይም። የራስሽን ታሪክና የራስሽን ስም ለመገንባት ኢንተርኔትና ማህበራዊ ድረገፆች በእጅጉ ጠቃሚ ናቸው በማለት እሷም እንደምትጠቀምባቸውና እንደምታደንቃቸው ትገልፃለች።
ሶፊያ ለኢትዮጵያ ያላት የወደፊት ተስፋ ብዙ ነው። ከፍተኛ የኢኮኖሚ እምቅ አቅሟን ተጠቅመው እድገትን እውን ሊያደርጉ የሚችሉ፣ በትምህርትና በፈጠራ ችሎታ የበለፀጉ ኢትዮጵያውያን ይታይዋታል። ኢትዮጵያዊያን ጥልቅ ሃይማኖታዊ ትውፊት የታደሉ በመሆናቸው፣  ስርዓትን የሚከተሉና የህግ የበላይነትን የሚያከብሩ ናቸው። ኢትዮጵያውያን ሰፊ የመናገር ነፃነት እንዲሁም ሰፊ የግል ኢንቨስትመንት ነፃነት እንዲኖራቸው ትመኛለች። በተለይ በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን፤ አገራቸውን ለመጥቀም የሥራ ፍሬያቸውንና ትምህርታቸውን ይዘው መምጣት ይፈልጋሉ። የኢንቨስትመንት ነፃነት በተሻለ ደረጃ እንዲስፋፋላቸውም ምኞቷ ነው።
ምንጭ፤-
www.ethiopianwomenunleashed..org

Monday, 07 April 2014 15:42

ሃገሬ ትንሳኤሽ

ክፉ ግዜሽ አልቆ
እንባ ከአይንሽ ደርቆ
ሰቀቀንሽ አልፎ
ጥቀርሻሽ ተገፎ
ጉዳትሽ ታክሞ
አጉል ስምሽ ቀርቶ
ብሩህ ፀሐይ ወጥቶ
ማቅሽን አውልቀሽ
ጥበብሽን ለብሰሽ
ጎጆሽን አሙቀሽ
አደይ ተከናንበሽ
ጤናዳም፣ አሪቲ፣ ቄጤማ ጎዝጉዘሽ
በጎችሽ ሳይጎድሉ ሁሉንም ሰብስበሽ
ክብርሽ ተመልሶ
ቃል ኪዳንሽ ደርሶ
ልጆችሽ ተዋደው
ተስማምተው - ተግባብተው
ስትስቂ
ስትስቂ
ስትስቂ የማየው
ሃገሬ ንገሪኝ ዘመኑ መቼ ነው?
ተጻፈ፡- ፯/፯/፳፻፭ ንጋት ፲፪፡ ፭

የሁለት ታላላቅ ግድቦች ወግ
ታላቁ የህዳሴ ግድብ እና ታላቁ ‹‹ሁቨር ዳም››

   የህዳሴው ግድብ ግንባታ የተጀመረበት 3ኛ ዓመት ሲከበር፤ ከስድስት ወር በፊት በአሜሪካ በነበረኝ ቆይታ የተደነቅሁበትን የሁቨር ግድብ አስታወሰኝ፡፡
እኛ ኢትዮጵያውያን የገባንበት ያህል ችግርና ውድቀት ባይገጥማቸውም፤ አሜሪካዊያን ያኔ በ1923 ዓ.ም ከባድ ቀውስና ጭንቀት ውስጥ ነበሩ። እኛ ከስልጣኔ ማማ ላይ ሳናውቀው ተንሸራተትን ከወደቅን ወዲህ፣ ለሺ አመታት ከከበበን ድቅድቅ ጨለማ ለመገላገል ስንመኝ ኖረናል፡፡ ጥንታዊውን የስልጣኔ ጉዞ እንደገና የሚያድስና የብልፅግና ዘመንን የሚያበስር ነገር እንፈልጋለን - የህዳሴ ግድብ ትርጉምም የዚህን ያህል ግዙፍ ነው - ‹‹ታላቅ ነበርን፤ ታላቅም እንሆናለን›› እንዲሉ፡፡
የሁቨር ግድብም እንዲሁ ለአሜሪካውያን ተቀራራቢ ትርጉም አለው፡፡ እስከ 20ያኛው ክፍለ ዘመን መባቻ ድረስ ለመቶ አመታት በስልጣኔና በብልጽግና ጐዳና ታይቶ የማይታወቅ ታሪክ የሰራችው አሜሪካ፣ ብዙም ሳይቆይ ነው በታላቅ የኢኮኖሚ ቀውስ የተመታችው፡፡ የ1920ዎቹ ዓመታት ለአሜሪካ ክፉ ዓመታት ናቸው፡፡ ብርሃኗ የደበዘዘባት፤ ፋና ወጊ መንፈሷ የቀዘቀዘባት ዘመን!
የረሃብና የግጭት አዘቅት ውስጥ ባይዘፈቁም፤ የስልጣኔና የብልጽግና ጉዟቸው ተብረክርኮ፤ የ‹‹ይቻላል›› መንፈስ የተዳከመባቸው አሜሪካዊያን፣ የጨለማ ድባብ ሲያንዣብብባቸው ጊዜ ህዳሴ አስፈለጋቸው፡፡ “ሁቨር ዳም” የዚያ ፍላጎት ውጤት ነው፡፡ በትግል ቋንቋ እንግለፀው ቢባል፤ “ብሶት የወለደው ጀግናው የአሜሪካ ህዝብ” እንደማለት ነው! እኛ ለአባይ የዘፈንለትን ያህል አሜሪካዊያን ለኮሮላዶ ወንዝ አላዜሙም፡፡ ነገር ግን እኛ ለአባይ ስንቆጭ እንደኖርነው፤ እነሱም በኮሮላዶ ወንዝ መቆጨታቸው አያጠራጥርም፡፡
ወንዙ ከአፍንጫቸው ስር እንደ ጅብራ ተገትሮ ሳይጠቀሙበት መፍሰሱ ሳያንስ፤ በየአመቱ ገጠር ከተማውን ሲያማርጥ በጐርፍ ያጥባቸዋል፡፡ በሸለቋማው ወንዝ፣ ከፍቅረኛው ተለያይቶ የቅርብ ሩቅ ለመሆን የተገደደ ጎረምሳ፤ “አንቺ ከአባይ ማዶ” እያለ እንደሚያንጎራጉረው ሁሉ፣ የኮለራዶ ወንዝም አሜሪካያውንን ሲያራርቅ ኖሯል፡፡
አሪዞናን ከወዲህ ማዶ፣ የኔቫዶ በረሃን ወዲያ ማዶ ሰንጥቆ የሚያልፈው የኮለራዶ ሸለቋማ ወንዝ፤ በርካታ ግዛቶችን እያቆራረጠ ይገሰግሳል፡፡ ዛሬ ግን እልም ካለው የኔቫዳ በረሃ ላይ ጉብ ካለችው ሽቅርቅሯ ላስ ቬጋስ ከተማ፣ ወደ አሪዞና በሚወስደው ምቹ መንገድ በመኪና ለሰላሳ ደቂቃ እንደተጓዙ፤ ፊት ለፊት ከአይንዎ ጋር የሚጋጨው ተራራና ገደል ሳይሆን ሰማይ ጠቀስ ግድብና ድልድይ ነው፡፡
በኦሪዞና ግዛት የፊኒክስ ከተማንና በኔቫዳ ግዛት ላስ ቬጋስን የሚያገናኘው ሰማይ ጠቀስ ድልድይ በየእለቱ በሰዎች ሲጥለቀለቅ ይውላል፡፡ “ከወንዝ ማዶ ያለሽው” እና “ከወዲያ ማዶ ያለኸው” እያሉ ናፍቆታቸውን የሚያንጐራጉሩ ፍቅረኞች አይደሉም በድልድዩ የሚተላለፉት፡፡ ሁቨር ዳምን ለማየት የሚመጡ ጐብኚዎች፣ እንጂ፡፡ ግድቡን ለመመልከት በየቀኑ የሚመጡ በርካታ ሺህ የዓለም ጐብኝዎች ረዥሙን ግድብ ላይ ላዩን አይተው አይመለሱም፤ ውስጥ ለውስጥም ይጐበኙታል፡፡ የኤሌክትሪክ ሃይል ማመንጫ ጣቢያዎቹ የሚገኙት ከግድቡ ስር መሬት ውስጥ በጥልቅ ቦታ ነው፡፡ በሊፍት ወደ መሬት ውስጥ ቁልቁል ብዙ ርቀት መግባት ያስፈልጋል፡፡
ሊፍት ከመያዛችን በፊት ከአስጐብኛችን አንደበት የወጡ ቃላት ፍርሃት ለቀቁብኝ፡፡ “ከመሬት በ5ሺህ ጫማ ርቀት ወደ ታች እንዘልቃለን፡፡ ይህ ግድብ ሲገነባ የዘጠና ስድስት ሰዎች ህይወት አልፏል” አለች፡፡
“አውቃችሁ ግቡበት” አይነት አባባልዋን እየሰማን በዝምታ ስንተያይ፤ እሷ በጣቷ የሊፍቱን መቆጣጠሪያ ተጫነች፤ ወደ መሬት እንብርት ይዞን እንዲሸመጥጥ፡፡ እንጀራዋ ነው፡፡ እንደ ባልደረቦቿ ጐብኚዎችን በቡድን እያሰባሰበች ስታስተናግድ ትውላለች፡፡ ከአንድ ሰዓት በላይ በሚፈጀው መስተንግዶ፤ በቀን አምስት ጐብኚ ቡድኖችን ተቀብላ ዙሪያውን ታስቃኛለች፡፡ ሰማይ ጠቀስ ግድቡንና ድልድዩን፤ እንደ አገር የተንሰራፋውን ሃይቅና ዙሪያ ገባውን ካስጎበኘች በኋላ፣ ነው የሃይል ማመንጫ ጣቢያውን ለማሳየት ቁልቁል ከአንድ ኪሎሜትር ጥልቀት በታች ይዛን የጠለቀችው፡፡ ወደ ምድር ስር የሚዘልቅ ባለ ሦስት መቶ ፎቅ ያህል እንደማለት ነው፡፡ ሳስበው አሁን ድረስ ያስፈራኛል። ከላያችን ላይ ግዙፍ ግድብ ብቻ ሳይሆን ግዙፍ ሃይቅ አለ፡፡ እዚያ ስር ነው፤ በየአመቱ 4.5 kwh የኤሌክትሪክ ሃይል የሚመነጨው፡፡ የኢትዮጵያ ጠቅላላ አመታዊ የኤሌክትሪክ ሃይል ከአንድ ግድብ ይመነጫል፡፡
በየአመቱ የ18 ሚሊዮን አሜሪካዊያን መኖሪያ አካባቢዎችን በጐርፍ እያጥለቀለቀ ከፍተኛ ጥፋት ሲያደርስ የነበረው ኮሎክራዶ ወንዝ፤ ዛሬ ለሚሊዮኖች የኤሌክትሪክና የብርሃን መፍለቂያ፤ ለሚሊዮኖች የመጠጥና የመስኖ ውሃ አስተማማኝ ምንጭ ሆኗል፡፡ እንደ አገር የሚሰፋው ሰው ሰራሽ ሃይቁም በዓለም ላይ የመጀመሪያው ትልቁ ሰው ሰራሽ ሀይቅ በመባል በመዝናኛነቱ ለመታወቅ በቅቷል፡፡ ነገር ግን፣ ግንባታው አልጋ በአልጋ አልነበረም፡፡ ለግድብ ግንባታ ተስማሚ የሆነ ቦታ ስላልተገኘ፣ የወንዙን አቅጣጫ ማስቀየር የግድ ነበር፡፡ የስራው ክብደት ራሱን የቻለ ፈተና ነው፡፡ ከሁሉም በፊት ግን የይገባኛል ውዝግቦችን በድርድር መፍታትና መስማማት ያስፈልግ ነበር፡፡ በርካታ ግዛቶችን የሚያካልለው ትልቅ ወንዝ፣ አቅጣጫውን እንዲቀይር ሲደረግ፤ በውሃ ክፍፍልና ድርሻ ላይ ከየግዛቱ ክርክሮች ተፈጥረዋል፡፡ እንዲያውም ውዝግቡ ከመካረሩ የተነሳ፣ የግድቡ ግንባታ ‹‹ህልም ሆኖ ይቀራል›› እስከመባል ደርሷል፡፡
ደግነቱ ስልጡን ሰዎች፣ እድሜ ልክ እየተወዛገቡ አይቀጥሉም፡፡ ይወያያሉ፤ ይደራደራሉ፡፡ ለዚህም ነው፤ የአሜሪካ 31ኛው ፕሬዚዳንት ኸርበርት ሁቨር ከየግዛቱ አስተዳዳሪዎችና ባለስልጣናት ጋር በመገናኘት ሚዛናዊ የውሃ ክፍፍል እንዲኖር የተወያዩት፡፡ አስጐብኚያችን ከ90 አመት በፊት ስለነበሩት ፕሬዚዳንት ስትናገር፤ የአጐቷን ታሪክ የምትተርክ ትመስላለች፡፡
“ኸርበርት ሁቨር ከፖለቲከኛነቱ በተጨማሪ መሃንዲስ ነው፡፡ ወግ አጥባቂ ቢሆንም ደግ ሰው ነው፡፡ የታታሪነቱ ያህል አሳ በማጥመድ መዝናናትን የሚወድ ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ፤ ‘የሰው ልጅ በአካባቢው የሚገኙ ተፈጥሯዊ ነገሮችን ወደ መልካምና ጠቃሚ ነገር የመለወጥ ችሎታ አለው’ የሚል ጠንካራ እምነትና ራእይ የያዘ ሰው ነው፡፡” … አስጎብኚያችን ፕሬዚዳንቱን በቅርብ የምታውቃቸው ሆኖ ሰተማኝ፡፡
የሆነ ሆኖ በውይይቱ ወደ ስምምነት ከተደረሰ በኋላ ነው፤ በአንድ በኩል ተራሮችን በድማሚት መናድና የወንዙን አቅጣጫ ማስቀየር፤ በሌላ በኩል በሸለቆ የተራራቁትን ተራሮችን ለማገናኘት የግድብ ግንባታ የተጀመረው፡፡
በሰው ልጅ ታሪክ ታላቁን ግድብ በመስራት እውቀትና ችሎታቸውን ለማሳየት የተዘጋጁት አሜሪካዊያን መሃንዲሶች ከፈተና አላመለጡም። የኔቫዳ በረሃ፣ የኛው ህዳሱ ግድብ ከሚገነባበት ከቤኒሻንጉል ክልል ባልተናነሰ የሙቀት መጠን የሚታወቅ ቦታ እንደመሆኑ፣ ለግዙፍ የኮንክሪት ስራ በፍፁም አይመችም፡፡ የፎቅ ግንባታ ላይ እንደሚታየው፤ ቀጫጭን ምሰሶዎችና ግድግዳዎችን በኮንክሪት መስራት አያስቸግርም፡፡ ትንሽ ውሃ ከተረጨበት ኮንክሪቱ ብዙም ሳይቆይ ይቀዘቅዛል። ግራና ቀኝ፣ ፊትና ኋላ፣ ላይና ታች የተደፈነ የኮንክሪት ተራራ ሲገነባ ግን፣ ኮንክሪቱ በፍጥነት የመቀዝቀዝ እድል የለውም፡፡
ኮንክሪቱ እስኪቀዘቅዝ እየጠበቀን እንስራ ከተባለ ግንባታው 100 ዓመት እንደሚፈጀ ነበር የተገመተው፡፡ የህዳሴው ግድብ ግንባታ ላይ ኮንክሪቱ እንዲቀዘቅዝ የሚደረገው ላዩ ላይ በረዶ በማፍሰስ ነው፡፡ የሁቨር ግድብ ሲገነባ ግን፣ እንደዛሬ በረዶ ማምረቻ ማሽን በቀላሉ የሚገኝ አልነበረም፡፡ ቢሆንም መሃንዲሶቹ ውሃ በመጠቀም ኮንክሪቱን የሚያቀዘቅዝ መላ ዘየዱ፡፡ ስራውም ሳይጓተት ቀጠለ፡፡ እንዲያውም ሰባት አመት ይፈጃል የተባለው ግንባታ ከታቀደለት ጊዜ ቀደም ብሎ በአምስት ዓመት ተጠናቀቀ፡፡  
ግድብ ለመስራት የፈሰሰው ሲሚንቶና ኮንክሪት፤ 4674 ኪሎ ሜትር ደረጃውን የጠበቀ ሰፊ የአስፓልት መንገድ ሊሰራ ይችላል፡፡ ከኢትዮጵያ እስከ ደቡብ አፍሪካ የሚዘልቅ አስፋልት መንገድ ማለት ነው፡፡ በምን ያህል ወጪ እንደተገነባ አትጠይቁኝ፡፡
ለካ በኛ አገር ብቻ ሳይሆን በአሜሪካም፣ ያኔ ድሮ ሁሉም ነገር ርካሽ ነበር፡፡ ለግድቡ የወጣው ገንዘብ 49 ሚሊዮን ዶላር ነው፡፡ በዛሬ ገንዘብ ቢሰላ ከቢሊዮን ዶላር ሳይበልጥ አይቀርም፡፡ በሦስት ፈረቃ ተፍ ተፍ ለሚሉት 3500 አሜሪካዊያን ሰራተኞች የሚከፈለው ደሞዝ፤ እንደ የሙያቸው ቢለያይም፣ ዝቅተኛው ክፍያ በቀን አራት ዶላር ነበር፡፡ ቀላል ይመስላል፡፡ በዛሬ ሂሳብ ከ100 ዶላር ሊበልጥ ይችላል፡፡
አስተማማኝ የኤሌክትሪክና የውሃ ምንጭ ከመሆን አልፎ፣ ለበርሃማው አካባቢ አዲስ ሕይወት የሚሰጥ ሰው ሰራሽ ሃይቅ ለመፍጠር የበቃው ግድብ ሲጠናቀቅ፤ ኸርበርት ሁቨር ስልጣን ላይ አልነበሩም። እንደመታደል ሆኖ የእኛው የቀድሞ ጠ/ሞኒስትር መለስ ዜናዊም የግድቡን የመሰረት ድንጋይ ጥለው ግንባታውን ቢያስጀምሩም መርቀው ለመክፈት ሳይታደሉ ህይወታቸው አልፏል፡፡
በኮሰራይ ወንዝ ላይ፣ በኛው ቋንቋ የመሰረት ድንጋይ በማስቀመጥ ግንባታውን ያስጀመሩት ሁቨር፤ የስልጣን ዘመናቸው በምርጫ ተቋጭቷል። በምትካቸው ስልጣን የተረከቡት ፕሬዚዳንት ፍራንክሊን ሩዝቬልት ናቸው፡፡ እ.ኤ.አ መስከረም 30ቀን 1935 ዓ.ም ግድቡን መርቀው ከፈቱት። “ቦልደርስ ዳም” ነበር የሚባለው፡፡ ስሙ የተለወጠው በ1947 የአሜሪካ ኮንግረስ ሁቨር ዳም ተብሎ እንዲሰየም ባሳለፈው ውሳኔ ነው፡፡ የኛ ግድብ ግን፣ ገና ሳይጀመር ነው ስሙ የተለወጠው፡፡ “ሚሌኒየም ግድብ” የሚለው ስያሜ ተቀይሮ “ህዳሴ” ግድብ ተብሎ የተሰየመ፡፡     
  አስጎብኛችን በመሬት ውስጥ ቆይታችን የአስራ ሁለት ደቂቃ ትንተናዋን ጨርሳ ወደ ምድር ወለል ለመውጣት ሽቅብ ስንገሰግስ ፍርሃቴ አላገረሸም። ‘አንድ ነገር ቢመጣኮ እዚሁ ድፍት ብለን መቅረታችን ነው’ የሚለው ስጋቴ ለቆኝ ወደሌላ ሃሳብ ተጉዣለሁ። ወደ ታላቁ የህዳሴ ግድብ!!  
የህዳሴው ግድብ ምርቱ ተትረፍርፎ፣ በድርቅና በረሃብ ለምትታወቀው አገራችን የጥንት ስልጣኔዋ እንዲታደስና የብልፅግና ዘመን እንዲበሰር ያደርግ ይሆን? የአገራችንን ገፅታ ይቀይር ይሆን? ግንባታው ሲጠናቀቅና እልፍ አእላፍት ሲጐበኙት፤ ኤሌክትሪክ ሲያመነጭና ለመስኖ ሲያገለግል ማየት ናፈቀኝ፡፡
“ይሁን!!” ብያለሁ፡፡ የህዳሴው ግድብ ሲጠናቀቅ ከአገር አልፎ ለጎረቤትም ያብራ!! ለመብላት የሚዘረጉ እጆች፣ ከአንድም ሶስት ጊዜ ጦም አይደሩ!! ስደትንና ድርቅን ያስወግዱ!!

        በአለም አቀፉ የሙዚቃ ኢንዱስትሪ የካበተ ልምድ ያላት አፍሪካ - አሜሪካዊቷ ኢትዮጵያ ሐብተማርያም፣ የታዋቂው የአሜሪካ የሙዚቃ ቀረጻ ኩባንያ የሞታውን ሪከርድስ ፕሬዚዳንት ሆና መሾሟን ዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ ገለጸ፡፡ የአለማችን ትልቁ የሙዚቃ ኩባንያ የሆነው ዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ፣ ከዚህ በፊት በስሩ ይተዳደሩ የነበሩትን ዴፍ ጃም ሪከርድስ፣ አይስላንድ ሪከርድስና ሞታውን ሪከርድስን እንደገና በማዋቀርና ራሳቸውን ችለው እንዲሰሩ በማድረግ፣ ኢትዮጵያ ሃብተማርያምን የሞታውን ሪከርድስ ፕሬዚዳንት አድርጎ በዚህ ሳምንት መሾሙን አስታውቋል፡፡እ.ኤ.አ በ2003 ታዋቂውን ዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ የተቀላቀለችው ኢትዮጵያ ሐብተማርያም፣ ጀስቲን ቢበርና ክሪስ ብራውንን ጨምሮ አለማቀፍ ዝና ያላቸውን በርካታ ታዋቂ ድምጻውያን፣ የሙዚቃ ደራሲያንና አርቲስቶችን ለኩባንያው በማስፈረም ተጠቃሽ ስራ የሰራች ሲሆን፣ ከ2011 አንስቶም የዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ ምክትል ፕሬዚዳንት እና የኧርባን ሚዩዚክ ሃላፊ በመሆን አገልግላለች፡፡
ዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕን በምክትል ፕሬዚዳንትነት በመራችባቸው አመታት፣ ሜሪ ጄ ብላይጄ፣ ፊፍቲ ሴንት፣ ኤሚኔየም፣ አሻንቲ፣ አይስ ኪዩብ፣ አር ኬሊና ሌሎች በርካታ የፕላቲኒየምና የግራሚ ተሸላሚ አርቲስቶችን ወደ ኩባንያው በመሳብ፣ ስኬታማነቷን ያስመሰከረችው ኢትዮጵያ ሐብተማርያም፣ ለረጅም አመታት በዘርፉ ተጠቃሽ ስራዎችን ሲያከናውን የቆየውን ሞታውን ሪከርድስ ወደተሻለ ትርፋማነት ታሸጋግራለች ተብሎ ስለታመነባት ነው በፕሬዚዳንትነት የተሾመችው፡፡
ሞታውን ሪከርድስ የማኔጅመንት፣ የማርኬቲንግና የማስታወቂያ ስራ አቅሙን የበለጠ በማሳደግ፣ ራሱን የቻለ አለማቀፍ የሪከርዲንግ ኩባንያ እንዲሆን ፣ ኢትዮጵያ ሐብተማርያም ከፍተኛ ሃላፊነት እንደተጣለባት የዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ መግለጫ ያሳያል፡፡
የዩኒቨርሳል ሚውዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈጻሚ ሉቺያን ግሬንጅ እንደተናገሩት፣በኢትዮጵያ ሐብተማሪያም የሚመራው ሞታውን ሪከርድስ፣ ተቀማጭነቱን እ.ኤ.አ ከ1972 ጀምሮ ለ25 አመታት ያህል  በርካታ ስራዎችን አሳትሞ ለአድማጭ ሲያቀርብበት በነበረው ሎሳንጀለስ በማድረግ፣ በዘርፉ አያሌ  ስራዎችን ያከናውናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ኢትዮጵያ ሐብተማርያም ከአዲሱ ሹመቷ በተጨማሪ፣ በዩኒቨርሳል ሚዩዚክ ፐብሊሺንግ ግሩፕ የኧርባን ሚዩዚክ ሃላፊነት ስራዋን ጎን ለጎን እንደምትቀጥል ተነግሯል፡፡

        ቦታው ለልማት ይፈለጋል ተብሎ ቤት ሲፈርስ፣መጠለያ አጥተው ቤተ-መንግስት ስር መኖር የጀመሩት  48 ቤት አልባዎች፤ሰሞኑን “በጅብ መንጋ ልንበላ ነው” ሲሉ ምሬትና አቤቱታቸውን ገለፁ፡፡ ከጅቦቹ ይከላከሉናል ብለን የሰበሰብናቸው ውሾችም በወረዳው ባለስልጣናት በመርዝ ስለተገደሉብን ከፍተኛ ስጋት ላይ ነን ብለዋል - ቅሬታ አቅራቢዎቹ።
 የወረዳ ስምንት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ደሳለኝ ደበሌ ስለጉዳዩ ጠይቀናቸው ሲመልሱ፤በወረዳው ሸራተንና ፓርላማ በመባል የሚታወቁ ሁለት ፕሮጀክቶች እንዳሉ ገልፀው፤ በሸራተን ፕሮጀክት ለመልሶ ማልማት 1319 ቤቶች ሲፈርሱ፣ምትክና ካሳ እየሰጠን መመሪያው የሚፈቅድላቸውን አስተናግደናል ብለዋል፡፡ በወረዳው ረጅም ዓመት ለኖሩ ምንም መረጃ የሌላቸው ከ60 በላይ ሰዎችም አስተናግደናል ይላሉ- ሥራ አስፈፃሚው፡፡ በሸራተን ዙሪያ በጥገኝነትና በተከራይነት ከ15-23 ዓመት እንደኖሩና የቀበሌ መታወቂያ እንዳላቸው የነገሩን  ቤት አልባዎች የወረዳ ኃላፊዎቹን ይወቅሳሉ፡፡ “ከዛሬ ነገ ቤት ይሰራላችኋል፤መጠለያ ተፈልጎ ትገባላችሁ” ሲሉን ቢቆዩም እስካሁም መፍትሄ አላገኘንም ይላሉ፡፡ አሁን ከቤቱም በላይ ሃሳብ የሆነባቸው የጅቦቹ ጉዳይ ነው፡፡ ጅቦች ከነጋ በኋላም እየመጡብን ከፍተኛ ስጋት ፈጥረውብናል ብለዋል - ነዋሪዎቹ፡፡
“ወረዳው ቀደም ሲል በእኛው ጉዳይ ከአዲስ አድማስ ጥያቄ ቀርቦለት ‘ከክፍለ ከተማው ጋር ተመካክረን የመጠለያ ቦታ አፈላልገን አግኝተናል’ የሚል ምላሽ ቢሰጥም እኛ ግን እስካሁን መፍትሄ አላገኘንም” ያሉት ስማቸውን መግለፅ ያልፈለጉ የአምስት ልጆች አባት፤ በላስቲክ ቤት ውስጥ መኖራቸውን በመቀጠላቸው  ጅቦች ስጋት እንደፈጠሩባቸው ጠቁመው፣ “ዜጎች እንደመሆናችን መንግስት መፍትሄ ይፈልግልን” ሲሉ ተማፅነዋል፡፡
የወረዳ ስምንት ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ደሳለኝ በበኩላቸው፣ “ከዚህ በፊት ጉዳዩን እየተመለከትን በወረዳው እንደመኖራቸው መንግስት የእነዚህን ዜጎች ችግር የመፍታት አቅም ይኖረዋል አይኖረውም የሚለውን ለክ/ከተማው አቅርበናል” ካሉ በኋላ በክፍለ ከተማው ወረዳ 14 ባለወልድ ጀርባ የቆርቆሮ መጠለያ እንደነበረና መጠለያው ከተቃጠለ በኋላ ቦታው ባዶ መሆኑን በማስረዳት፣ እዚያ ቦታ ላይ የቆርቆሮ መጠለያ እንዲሰራ አመልክተን ነበር ይላሉ፡፡  “በወቅቱ የነበሩት የክ/ከተማው ዋና ስራ አስፈፃሚ፣ ከካቢኔ አባላት ጋር ተመካክረው ምን ያህል በጀት እንደሚፈጅ ሰርተን እንድናቀርብ ገልፀው ነበር” ያሉት ስራ አስፈፃሚው፣ በዚህ መሰረት የወረዳው ኮንስትራክሽንና ቤቶች ልማት ባለሙያዎች ምን ምን እንደሚያስፈልግ ሰርተው፣ ለክ/ከተማው አቅርበው ነበር ይላሉ፡፡ ይሁን እንጂ በ2005 ዓ.ም በተካሄደው ምርጫ የመዋቅር ለውጥ በመደረጉና የቀድሞው የክ/ከተማው ስራ አስፈፃሚ ከቦታው በመነሳታቸው፣ የእነዚህ ዜጎች ጉዳይ ሊቀጥል እንዳልቻለ አቶ ደሳለኝ አስረድተዋል፡፡
“በሸራተን ፕሮጀክት ውስጥ ቤት የሚጠይቁት ቤት የማግኘት መብት ኖሯቸው ሳይሆን በወረዳው ብዙ ጊዜ ስለቆዩ የሚቻል ነገር ካለ ብለን የጀመርነው ነበር” ያሉት ዋና ስራ አስፈፃሚው፣ ነገር ግን ገና ለገና ቤት እናገኛለን በሚል ከጎዳና ላይ እየገቡ ላስቲክ ቤት እየሰሩ እንደሚቀመጡና ረጅም አመት የኖሩትን ለመለየት በተደረገው ማጣሪያ 31 አባወራዎች መኖራቸውን፣እነዚህንም ከነቤተሰቦቻቸው በፎቶ አስደግፈው መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡ የጅቦቹን ጉዳይ በተመለከተ፣ ኮተቤና በአካባቢው ለመንገድ ስራ ጫካ ሲነካ እየሸሹ የሚመጡ መሆኑን ገልፀው፣ በሸራተን ፕሮጀክት ብቻ ሳይሆን በባለወልድ አካባቢ ለነዋሪዎች ስጋት በመሆናቸው ወረዳው ከደንና የዱር እንስሳት ልማትና ጥበቃ ጋር በመመካከር፣መፍትሄ በመፈለግ ላይ እንደሆኑ ሥራ አስፈፃሚው ተናግረዋል፡፡
“ወደፊት በወረዳው ኮንዶሚኒየም ቤት ደርሷቸው የሚለቀቁ ቤቶች ሲኖሩ ቅድሚያ ይሰጣቸዋል” ያሉት ስራ አስፈፃሚው፤ በዚህ ጊዜ እንዲህ እናደርግላቸዋለን ለማለት እንደሚቸገሩና ለክ/ከተማው ሲወስን ጉዳያቸው እንደሚታይ ተናገረዋል፡፡
ሐምሌ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ለንባብ በበቃው አዲስ አድማስ ጋዜጣ “ትራሳቸውን ቤተ-መንግስት ግርጌያቸውን ሸራተን ያደረጉ ቤት አልባዎች” በሚል ርዕስ ስለእነዚሁ 48 ቤት አልባ አባወራዎች መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን በወቅቱ የወረዳ ስምንት ዋና ስራ አስፈፃሚ ከክ/ከተማው ጋር በመነጋገር፤ ለቤት አልባዎች የቆርቆሮ መጠለያ ለመስራት ቦታ በመፈለግ ላይ እንደሆኑ ገልፀውልን ነበር፡፡

   ሰሞኑን በቤልጂየም መዲና ብራሰልስ በተካሄደው የአፍሪካ አውሮፓ ጉባኤ ላይ የተገኙት የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ነቢል ፋሃሚ፤ ከጉባኤው ጎን ለጎን  ታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ላይ ጫና ለማሳደር፣ ከመንግስታቱ ድርጅት ዋና ፀሀፊ ባን ኪ ሙንና ከአውሮፓ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ካትሪን አሽተን ጋር ተወያዩ፡፡
የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር፤ በብራሰልስ  የባን ኪ ሙን መኖሪያ ቤት ተገኝተው በታላቁ የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ ዙሪያ የተወያዩ ሲሆን ግብፅ በኢትዮጵያ ላይ ጫና ለማሳደር የጀመረችው ዓለም አቀፍ እንቅስቃሴ አካል ነው ተብሏል፡፡ ጉባኤው ከመጀመሩ አንድ ቀን ቀደም ብሎም ሚኒስትሩ ከአውሮፓ ህብረት የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ካትሪን አሽተን ጋር ተመሳሳይ ውይይት ማድረጋቸው ታውቋል፡፡ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ነቢል ፋሂም፤ እዚያው ብራሰልስ ካገኟቸው የኢትዮጵያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶክተር ቴዎድሮስ አድሀኖም ጋርም ተወያይተዋል፡፡ የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ ባለፈው ሰኞ ባወጣው መግለጫ፤“የግብፅን የውሀ ደህንነት ለማስጠበቅ የተቀናጀ የድርጊት መርሀ ግብር ተነድፏል፣ ጉዳዩም ደረጃ በደረጃ እየተሄደበት ይገኛል፣ ይህን የሚያስፈፅም ልዩ የህግ ኮሚቴ ተቋቁሟል፡፡ ግብፅ በአባይ ጉዳይ አዲስ ፋይል አታወጣም፡፡  አባይ የብሔራዊ ደህንነት ጉዳይ ስለሆነ ፖለቲካዊ፣ ህጋዊና  የቴክኒክ ጉዳዮችን ያካተተ መርሀ ግብር ተነድፏል” ብሏል፡፡
በሌላ በኩል በግብፅ የኢትዮጵያ አምባሳደር መሀሙድ ድሪር በአደራዳሪዎች ዙሪያ ሰሞኑን በሰጡት አስተያየት፤ “ግብፅ እና ኢትዮጵያ በግድቡ ዙሪያ ከራሳቸው ውጪ አደራዳሪ አይፈልጉም” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

         የራሺያ የጦር ሃይል የዩክሬንን ድንበር ሰብሮ፣ ክረሚያ የመግባቱን ሰበር ዜና ድፍን ዓለሙ የሰማው በድንጋጤና በመገረም ነበር፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን የራሺያ ድርጊት ምንም አይነት አስደንጋጭም ሆነ አስገራሚ ነገር አልነበረውም፡፡ የራሺያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን በዩክሬን ላይ የፈፀሙትን አይነት ድርጊት ምቹ ጊዜና አጋጣሚ ካገኙ ከመፈፀም እንደማይመለሱ ያዘጋጁትን እቅድ እንደ ሀገር ምስጢር ጨርሶ ደብቀውት አያውቁም፡፡
ከዛሬ አስራ አምስት በፊት ነሐሴ 16 ቀን 1999 ዓ.ም በፕሬዚዳንት ቦሪስ የልሲን የራሺያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው የተሾሙት ቭላድሚር ፑቲን፤ አዲሱን ሹመታቸውን ባፀደቀላቸው የራሺያ ዱማ (ፓርላማ) ፊት ቀርበው ንግግር አድርገው ነበር፡፡ ያኔ ያደረጉት ንግግር ለወጉ ያህል የሚደረግ ተራ ንግግር ሳይሆን በስልጣን ዘመናቸው ሊያከናውኑት የሚፈልጉትን ዝርዝር የስራ እቅዳቸውን የሚጠቁም ነበር፡፡
ቭላድሚር ፑቲን ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በተሾሙበት ወቅት ራሺያ ውቃቤ ርቋት ነበር፡፡ መቸም ቢሆን ለማንም በምንም አይረታም እየተባለ ይነገርለት የነበረው የራሺያ ጦር፣ ጠቅላላ ህዝቧ ራሺያ ካሰማራችው የጦር ሃይል ብዛት በእጅጉ በሚያንሰው በቺቺኒያ በአሳፋሪ ሁኔታ ተሸንፎ ነበር።
ቀደም ባለው ጊዜ የራሺያ ዋነኛ አጋርና የዋርሶ ጦር ቃል ኪዳን ድርጅት አባላት የነበሩ ሶስት የምስራቅ አውሮፓ ሀገራት፣ የኔቶ አባል ሀገር በመሆናቸው የምዕራቡን አለም ህብረት ክልል አፍንጫዋ ስር አድርሰውት ነበር፡፡ ራሺያን ከፍ ያለ ችግር ውስጥ የከተታትን ይህን ምስቅልቅል በቁርጠኝነት በመታገል እልባት ያበጁለታል ተብለው በከፍተኛ ተስፋ የተጠበቁት ፕሬዚዳንት ቦሪስ የልሲንም የመሪነት ነገር አለሙን ሁሉ እርግፍ አድርገው ትተው፣ ገና ሰማይና መሬት በቅጡ ሳይላቀቅ፣ ቮድካ በመጨለጥ ጥንብዝ ብሎ መስከርን ስራዬ ብለው የያዙበት፣ በዚህም የተነሳ ጤናቸው ክፉኛ ተቃውሶ ጐምላላው ሞት ከዛሬ ነገ ወሰድኳቸው እያለ የሚያስፈራራበት ወቅት ነበር፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ፑቲን ግን ለዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ ችግር መፍትሔ ይሆናል ያሉትን መላ አበጅተው በልቦናቸው ይዘው ነበር፡፡ እናም የጠቅላይ ሚኒስትርነቱን ስልጣናቸውን በሙሉ ድምጽ ባፀደቀላቸው የራሺያ ዱማ ፊት ቀርበው ባደረጉት ንግግር እንዲህ አሉ፤ “መንግስት መስራት ያለበትን ስራዎች ሁሉ በዚህ ንግግሬ ዘርዝሬ አልጨርሰውም፡፡ የሆኖ ሆኖ አንድ ነገር ግን በእርግጠኝነት አውቃለሁ፡፡ ከላይ ወደታች ያለው የእዝ ሰንሰለት ሳይጠናከር፣ በመላው ራሺያ መሰረታዊ ስርአት ሰፍኖ ጥብቅ የሆነ ስነምግባር ሳይጠበቅ፣ አንዱ ስራ እንኳ ይሰራል ማለት ዘበት ነው፡፡”
ጠቅላይ ሚኒስትር ፑቲን የሀገራቸውን የራሺያን ነገር ሲያስቡ በእጅጉ የሚቆጩበት ሌላም ጉዳይ ነበራቸው፡፡ ቭላድሚር ፑቲን የሶቪየት ህብረት ዝናና ተፈሪነት ሰማይ በነካበት ዘመን የተወለዱ የሶቪየት ህብረት ወርቃማው ዘመን ልጅ ናቸው። ያኔ እሳቸው በተወለዱበት በ1952 ዓ.ም ሶቪየት ህብረት በሁለተኛው የአለም ጦርነት ወቅት የናዚ ጀርመንን ጦር ሃይል እንዴት እንዳሸነፈች ዝናዋ አለመጠን ገዝፎ የሚተረክበት ጊዜ ነበር፡፡
ያ ወቅት ሶቪየት ህብረት ስፑትኒክ የተባለችውን መንኮራኩሯን ወደ ጠፈር ያመጠቀችበት፣ ሃይድሮጅን ቦንብን መስራት የቻለችበት፣ ዩሪ ጋጋሪን የተባለውን ጠፈርተኛዋን ወደ ጠፈር በመላክ በዓለም ቀዳሚ የሆነችበት፣ ላይካ የተባለውን ውሻም ወደ ጠፈር በመላክ ከአለም አንደኛ የተባለችበት ወርቃማ የዝናና የክብር ጊዜ ነበር፡፡
በቀጣዮቹ አመታትም በ1956 ዓ.ም በሀንጋሪ፣ በ1968 ዓ.ም ደግሞ በቼኮዝሎቫኪያ የተቀሰቀሰውን “ፀረ - አብዮት” አመጽ፣ ዝነኛውን ቀዩን ጦሯን አለአንዳች ማወላወል አዝምታ ሰጥ ረጭ በማድረግ፣ ባለብረት ክንድ ሀገር መሆኗን ያስመሠከረችበት ወቅት ነበር፡፡
ቭላድሚር ፑቲን ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በተሾሙበት ወቅት የነበረችው ሀገራቸው ግን በዓለም አቀፉ መድረክ የነበራት ቦታ ከድሮ ዝናና ክብሯ በእጅጉ የራቀ፣ እዚህ ግባ የማይባል ዝቅተኛ ቦታ ነበር፡፡ እንደእውነቱ ከሆነ፣ በወቅቱ የአለማችን የፖለቲካ መድረክ ራሺያን ከመሪ ተዋንያኖች ተራ አውጥቷት፣ የአለም ህዝብም ረስቷት ነበር፡፡
ለጠቅላይ ሚኒስትር ቭላድሚር ፑቲን እንዲህ ያለው የራሺያ አለማቀፋዊ ሁኔታ መቸም የማይበርድ የእግር እሳት ነበር፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው እስከተሾሙበት ጊዜ ድረስም ይህን ሁኔታ ለመለወጥ የሚችሉበትን “ቅዱስ አጋጣሚና ቀን” ለዘመናት ሲመኙ ኖረዋል፡፡
ልክ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው እንደተሾሙም ያ ሲመኙት የኖሩት ቀን እንደመጣላቸው በልባቸው አመኑ፡፡ እናም አንዳችም ጣጣ ሳያበዙና በዲፕሎማሲያዊ አነጋገር ነገር ሳያወሳስቡ ለዱማው እንዲህ በማለት እቅጩን ተናገሩ፣ “ራሺያ ለአያሌ ዘመናት ገናናና ታላቅ ሀገር ሆና ኖራለች፡፡ ወደፊትም ትኖራለች፡፡ የራሺያ የግዛት አንድነት ጉዳይ ለድርድር የሚቀርብ  አይደለም፡፡ የግዛት አንድነታችንን በሚዳፈር በማንኛውም አካል ላይ ጠንካራ እርምጃ እንወስዳለን፡፡ በቀድሞው የሶቭየት መሬትም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ላይ ህጋዊ የሆነ የብሔራዊ ጥቅም ጥያቄ ሁሌም ቢሆን አለን፡፡ በዚህ ረገድ የብሄራዊ ጥቅም ማስጠበቂያ ክንዳችን ለአፍታም ቢሆን መዛል የለበትም፡፡ እኛ የምናቀርበው ጥያቄም ሆነ አስተያየት በሌሎች ዘንድ ተንቆ ችላ እንዲባል መቸም ቢሆን መፍቀድ የለብንም፡፡”
ይህ ንግግር ቭላድሚር ፑቲን የራሺያን የውስጥና የውጪ ችግሮች ያስወግዳል ብለው አምነውበት ያወጡት እቅድ ዝርዝር መግለጫ ነው፡፡ ይህንን ንግግራቸውን ያደረጉትም በምስጢርና ለቁልፍ የስራ ባልደረቦቻቸው ብቻ አልነበረም፡፡ ይልቁንም ለመላው ዓለምም ጭምር እንጂ፡፡
ይህ የፑቲን እቅድ በእጅጉ የተስማማት የመሰለችው የራሺያ የስልጣን አድባርም ከፍ ባለ ልግስና ፊቷን አዙራላቸዋለች፡፡ ከጠቅላይ ሚኒስትርነት ወደ ፕሬዚዳንትነት ስታሸጋግራቸው የመንፈቅ ጊዜ እንኳ አልፈጀባትም፡፡ ከ2008 እስከ 2012 ዓ.ም በፕሬዚዳንት ዲሚትሪ ሜድቬዴቭ የስልጣን ዘመን ለሁለተኛ ጊዜ በጠቅላይ ሚኒስትርነት ከማገልገላቸው በቀር እነሆ ዛሬም ድረስ የፕሬዚዳንትነት ስልጣኑን ባርካላቸዋለች፡፡
ቭላድሚር ፑቲን በንግግራቸው በግልጽ እንዳስቀመጡት፤ የሀገር ውስጥ ፖሊሲያቸው በምድረ ራሺያ መረጋጋትን ማስፈንና ጠንካራ ከላይ ወደታች የሚፈስ የእዝ ተዋረድን ማረጋገጥ ላይ ሲያተኩር፣ የውጭ ፖሊሲያቸው ደግሞ በዋናነት ራሺያን ወደ ቀድሞ ገናና ዝናና ክብሯ በመመለስ፣ በዓለም አቀፍ የፖለቲካ መድረክ መሪ ተዋናይነት ዳግመኛ መመለስን ዋነኛ ግቡ ያደረገ ነው፡፡
መላው ዓለም ያኔ እንዲያ በግልጽና በዝርዝር የወደፊት እቅዳቸውን ያቀረቡበትን ንግግር በጥሞና አዳምጧቸውና አስታውሶት ቢሆን ኖሮ፣ ዛሬ ጦራቸውን ወደ ዩክሬን ሲያዘምቱ አይቶና ሰምቶ ክፉኛ ባልደነገጠ ነበር፡፡
ቭላድሚር ፑቲን ግን የስልጣን ዘመናቸውን አሀዱ ብለው ከጀመሩበት በነሐሴ 16 ቀን 1999 ዓ.ም ጀምሮ፣ ከመስከረም 11 ቀን 2001 ዓ.ም የአሜሪካ የሽብር ጥቃት እስከ አሁኑ የዩክሬን አብዮት ድረስ ከላይ የጠቀስኳቸውን የሀገር ውስጥና የውጭ ፖሊሲያቸውን ለማሳካት፣ ታሪክ የፈጠረላቸውን አጋጣሚዎች ሁሉ አለአንዳች ማመንታት ለመጠቀም ሞክረዋል፡፡ ስልጣናቸውን ለመቀናቀን ሞክረዋል ከተባሉት የቀድሞው የራሺያ ቁጥር አንድ ከበርቴ ሙሚካኤል ኮዶሮቭስኪ እስከ የቸቺኒያ አማጺያን ድረስ ያሉትን “አፈንጋጮች” እንደ ብረት በጠነከረው ክንዳቸው ልክ በማስገባት የሀገር ውስጥ መረጋጋት ፈጥረዋል፡፡
በዓለም አቀፍ የፖለቲካ መድረክ ላይም ከሁለተኛው ዙር የኢራቅ ወረራ እስከ ሶሪያ ህዝባዊ አመፅ ድረስ በተካሄዱት አለምአቀፍ የፖለቲካ መድረኮች፣ ራሺያ ከመሪ ተዋንያኖች አንዱ ሆና መተወን ችላለች፡፡
ይህ ሁሉ ግን የቆፍጣናውና የብሔርተኛውን የፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲንን ልብ ሊሞላው አልቻለም፡፡ የታላቁ አባት ሀገር የሲቪየት ራሺያ ግንባታ በፖለቲካው ብቻ ሳይሆን በግዛትም በደንብ መካሄድ ይኖርበታል፡፡ “በቀድሞው የሶቪየት መሬትም ሆነ በሌሎች ቦታዎች ላይ ህጋዊ የሆነ የብሔራዊ ጥቅም ጥያቄ ሁሌም ቢሆን አለን። በዚህ ረገድ የብሔራዊ ጥቅም ማስጠበቂያ ክንዳችን ለአፍታም ቢሆን መዛል የለበትም፡፡” ይህን የቭላድሚር ፑቲን ታሪካዊ ንግግር መቼም ቢሆን ልንረሳው አይገባም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፤ የአሜሪካንና የአውሮፓ ህብረትን ዛቻና ማዕቀብ ከምንም ሳይቆጥሩ የዩክሬን አካል የነበረችውና ትውልደ ራሺያውያን የሚበዙባት የክረሚያ ግዛት፣ የታላቁ አባት ሀገር ሶቪየት ራሺያ አባል እንድትሆን ያደረጉት ለምን እንደሆነ በወጉ ልንረዳው የምንችለው ይህን ንግግራቸውን በሚገባ ማስታወስ ከቻልን ብቻ ነው፡፡
እንግዲህ ግራም ነፈሰ ቀኝ፣ ፕሬዚዳንት ፑቲን በዩክሬንና በክሚያ ላይ የፈፀሙት ድርጊት፤ ከዚህ በፊት የአፍሪካ ችግር ብቻ ተደርጎ ይቆጠር የነበረው በተለያዩ ሀገራት ተከፋፍለው የሚኖሩ አንድ አይነት ህዝቦች፣ በአንድ ሀገር ውስጥ ተጠቃለው ለመኖር የሚያደርጉት ትግል፣ (irridentism) አዲሱ የአለማችን የ21ኛው ክፍለ ዘመን ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ችግር ሆኖ በዓለም አቀፍ የፖለቲካ መድረክ ላይ ብቅ እንዲል አድርገውታል፡፡
ይህ ጉዳይ ደግሞ በተለይ በባልቲክ ሀገራት ዘንድ ከፍተኛ ጭንቀትን ፈጥሯል፡፡ ይህ ደግሞ አለምክንያት አይደለም፡፡ ለምሳሌ ላቲቪያና ሊቱዋኒያ ከጠቅላላው በጠቀወላላው ህዝባቸው 30 በመቶ የሚሆኑት ትውልደ ራሺያውን ሲሆኑ በኢስቷኒያ ደግሞ ቁጥራቸው 25 በመቶ ይሆናል። አሁን ትልቁ ጥያቄ የፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ቀጣይ እርምጃና የእነዚህ አገሮች እጣ ፈንታ ምን ይሆናል የሚለው ነው፡፡

Monday, 07 April 2014 15:21

ፑቲንን በአጭሩ

ፕሬዚደንት ቭላድሚር ቭላድሚሮቪች ፑቲን፤ የፋብሪካ ሠራተኛ ከነበሩት እናታቸው ማርያ ኢቫኖቫ ፑቲና እና የሶቪየት ህብረት ባህር ሃይል ወታደር ከነበሩት አባታቸው ቭላድሚር ስፒሪዶኖቪች ፑቲን ቀድሞ ሌኒንግራድ በመባል በምትጠራው ቅዱስ ፒተርስበርግ ከተማ እ.ኤ.አ ጥቅምት 7 ቀን 1952 ዓ.ም ተወለዱ፡፡
ከመኖሪያ ቤታቸው አቅራቢያ በሚገኘው የባስኮቭ ትምህርት ቤት የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ካጠናቀቁ በኋላ፣ ለከፍተኛ ትምህርት ወደ ሌኒንግራድ ዩኒቨርሲቲ አመሩ፡፡ በዚህ ዩኒቨርሲቲ የህግ ትምህርት ቤት፣ የአለም አቀፍ ህግና ኢኮኖሚክስ ትምህርታቸውን ከተከታተሉ በኋላ በ1975 ዓ.ም ተመርቀው ወጡ፡፡
ቭላድሚር ፑቲን፤ አባታቸው ያገለግሉበት በነበረው የሶቪየት ህብረት የባህር ሃይል ውስጥ ኬጂቢ ተብሎ ከመቋቋሙ በፊት ኤንኬቪዲ በሚል ይጠራ በነበረው የሶቪየት ህብረት የደህንነትና የስለላ ድርጅት ውስጥ አባል እንደነበሩ ከልጅነታቸው ጀምሮ በሚገባ ያውቁ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የአባታቸውን ፈለግ በመከተል ሰላይ ለመሆን ምንም አይነት ፍላጐት አልነበራቸውም። ያኔ የነበራቸው ከፍተኛ ፍላጐት የስድስተኛ ክፍል ተማሪ ሳሉ ጀምረውት አለመጠን ፍቅር ባሳደረባቸው የጁዶ ስፖርት በመግፋት፣ በምድረ ሶቪየት ህብረት ከፍተኛ ዝናን መጐናፀፍ ነበር፡፡
የዘጠነኛ ክፍል ተማሪ በነበሩበት ወቅት ግን እንዲህ ሆነ፡፡ የሶቪየት ህብረት የማስታወቂያ ሚኒስቴር የስለላ ታሪክ ያለው ተከታታይ ፊልም ለህዝቡ በቴሌቪዥን ማቅረብ ጀመረ። እንደማንኛውም የሶቪየት ህብረት ዜጋም ወጣቱ ቭላድሚር ፑቲን ይህንን ፊልም ስራዬ ብለው መከታተል ጀመሩ፡፡ ሳያስቡት ግን በወቅቱ በሶቪየት ህብረት ታዋቂ የፊልም ተዋናይ የነበሩት ቪያችስላቭ ቲኮኖቭና ጆርጂ ዚህዞኖቭ ይተውኑት በነበረው የሰላይ ገፀ - ባህርያት በከፍተኛ ፍቅር ወደቁ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮም በፊልም እንዳዩዋቸው ሰላዮች መሆን የቀንም ሆነ የለሊት ህልማቸው ሆነ፡፡
በ1975 ዓ.ም ከሌኒንግራድ ዩኒቨርሲቲ ተመርቀው በወጡ ልክ በሁለተኛ ወራቸውም የሶቪየት ህብረት የስለላ ድርጅት ኬጂቢን በጀማሪ ሰላይነት ተቀላቀሉ፡፡ ቭላድሚር ፑቲን ምርጥ ሰላይ ለመሆን የነበራቸው ከፍተኛ ምኞትና ህልም እንዲሁ መና አልቀረባቸውም። በብዙ የኬጂቢ ሰላዮች ዘንድ እምብዛም ባልታየ ሁኔታ የስለላ ብቃታቸውን ማስመስከር የቻሉት ፑቲን፤ ባጭር ጊዜ ውስጥ ትከሻቸውን ለኮሎኔልነት ማዕረግ አበቁት፡፡ ሰውየው በዚህ ብቻ አላበቁም። በ1986 ዓ.ም በያኔዋ ምስራቅ ጀርመን የኬጂቢ ቢሮ ሃላፊ በመሆን ለመሾም ችለዋል፡፡
በ1990 ዓ.ም የያኔዋ ሶቪየት ህብረት ስትፈራርስ፣ ለ16 አመታት በከፍተኛ ብቃት ያገለገሉበትን ኬጂቢን በጡረታ ተሰናብተው በመውጣት፣ በራሺያ የፖለቲካ መድረክ የእጣ ፈንታቸውን ለመሞከር ጓዛቸውን ቀርቅበው ወደ ትውልድ ከተማቸው ወደ ቅዱስ ፒተርስበርግ አቀኑ፡፡
ቭላድሚር ፑቲን የፖለቲካውን አለም ለመቀላቀል ወስነው፣ በ1990 ዓ.ም ማብቂያ ላይ ወደ ሌኒንግራድ ወይም ቅዱስ ፒተርስበርግ ከተማ ያመሩበት እግራቸው እርጥብ ነበር። እዚያ እንደደረሱ በመጀመሪያ ያገኙት በሌኒንግራድ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ በነበሩበት ወቅት አስተማሪያቸውና ዋና ወዳጃቸው የነበሩትን አናቶሊ ሶብቸክን ነበር፡፡ ሁለቱ በተገናኙበት ወቅት ደግሞ የቀድሞው መምህራቸው ፕሮፌሰር አናቶሊ ሶብቸክ የቅዱስ ፒተርስበርግ ከንቲባ ነበሩ፡፡ ከአራት ቀናት በኋላም ከንቲባ አናቶሊ ሶብቸክ፣ ቭላድሚር ፑቲንን የአለም አቀፍ ጉዳዮች ዋና አማካሪያቸው አድርገው ሾሟቸው፡፡ ከንቲባ አናቶሊ ሶብቸክ በ1996 ዓ.ም በተደረገው የከንቲባነት ምርጫ በድጋሚ ለመመረጥ ያደረጉት ጥረት ሳይሳካ ቀርቶ በመሸነፋቸው ቭላድሚር ፑቲን የአማካሪነት ስራቸውን ለመልቀቅ ተገደው ስራ ፈት ለመሆን በቁ፡፡
ቭላድሚር ፑቲን በስራ ፈትነት ሁለት ወራት ካሳለፉ በኋላ ግን በክሬምሊን ቤተመንግስት የፕሬዚደንታዊ ንብረቶች አስተዳደር መምሪያ ሃላፊ የነበሩት የፓቬል ቦሮዲን ምክትል በመሆን እንዲያገለግሉ ጨርቄን ማቄን ሳይሉ ባስቸኳይ ወደ ሞስኮ እንዲመጡ፣ ፕሬዚደንት ቦሪስ የልሲን ጥሪ አቀረቡላቸው፡፡ መጋቢት 26 ቀን 1997 ዓ.ም ፕሬዚደንት የልሲን፤ ቭላድሚር ፑቲንን ምክትል የቢሮ ሃላፊ አድርገው ሾሟቸው፡፡
በቀጣዩ አመት ሐምሌ 25 ቀን 1998 ዓ.ም ቭላድሚር ፑቲን ከኬጂቢ በኋላ እንደ አዲስ የተቋቋመውና ኤፍኤስ ቢ በመባል የተሰየመው የራሺያ የደህንነትና የስለላ ድርጅት ሃላፊ እንዲሆኑ በፕሬዚደንት ቦሪስ የልሲን ተሾሙ፡፡
በዚህ ሃላፊነት እስከ መጋቢት 29 ቀን 1999 ዓ.ም ድረስ ካገለገሉ በኋላ፣ ነሐሴ 9 ቀን 1999 ዓ.ም እንኳን ሌሎች ራሳቸው ቭላድሚር ፑቲንም ጨርሶ ባላሰቡትና ባልገመቱት ሁኔታ በቮድካ ጨላጭነታቸው የታወቁትና ጤናቸው ከመቸውም ጊዜ በላይ አላወላዳ ያላቸው ፕሬዘደንት ቦሪስ የልሲን፤ የራሺያ ጠቅላይ ሚኒስትር አድርገው ሾሟቸው፡፡ ቭላድሚር ፑቲን ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው በተሾሙ አምስት ወር እንኳ ሳይሞላቸው ታህሳስ 27 ቀን 1999 ዓ.ም ድንገት ስልጣናቸውን የለቀቁትን ፕሬዚዳንት ቦሪስ የልሲን በመተካት የራሺያ ጊዜአዊ ፕሬዚደንት ለመሆን ቻሉ፡፡ የፕሬዚዳንትነት ስራቸውን አሀዱ ብለው የቀደሱትም በዚሁ እለት የቀረበላቸውንና ፕሬዚደንት ቦሪስ የልሲን ከነቤተሰባቸው በምንም አይነት የወንጀል ክስ እንዳይጠየቁ የሚደነግገውን ፕሬዚዳንታዊ አዋጅ በፊርማቸው በማጽደቅ ነበር፡፡

Monday, 07 April 2014 15:17

ለማይስቅ ውሻ ነጭ ጥርስ

ለማይገላመጥ ዶሮ ቀይ ዐይን ይሰጠዋል!
(የሚጬነ ከናስ አቻ ቦታ እሜስ ዴሬቄነ ኩቶስ አይፌ ዞኡዋ እሜስ)
የወላይታ ተረት

ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ደቃቃ ጥንቸል፤ እህል ውሃ ፍለጋ በጫካ ውስጥ ስትዘዋወር፤ አንድ ዝንጀሮ ታገኛታለች፡፡ ጥንቸሏ ግዙፍ ስላልሆነች በየቅጠላ ቅጠሉ ውስጥ እየተሹለከለከች መሄድ እንደምትችል ዝንጀሮ ያውቃል፡፡ ሆኖም አንድ ምክር ሊመክራት ፈልጓል፡፡
“እመት ጥንቸል! የረዥም ጊዜ ወዳጅነታችንን መሰረት በማድረግ ምክር ልለግስሽ እፈልጋለሁ” አላት፡፡
ጥንቸልም፤
“ምን ዓይነት ምክር? ስትል ጠየቀችው”
ዝንጀሮም፤
“ይህን ጫካ አትመኝው፡፡ ሰሞኑን አዳኞች መጥተው ለአውሬ ማጥመጃ የሚሆን ትላልቅ ጉድጓድ ሲቆፍሩ እኔ ዛፍ ላይ ሆኜ አይቻቸዋለሁ፡፡ ስለዚህ ጫካው እንደድሮው ሰላም መስሎሽ ወዲህ ወዲያ አትበይ”
ጥንቸልም፤
“አመሰግናለሁ፡፡ የወጥመዱን የሰሩት ለእኔ አይመስለኝም፡፡ እንደ አንበሳ፣ እንደነብር፣ እንደዝሆን ላሉት እንጂ እንደኔ ቀጫጫ ለሆነ ፍጡር አይደለም፡፡ ባጋጣሚ ጉድጓድ ውስጥ ብወድቅም መውጫ ብልሃት አላጣም!” ትለዋለች፡፡
ዝንጀሮም፤
“እንግዲህ የወንድምነቴን መክሬሻለሁ፡፡ ብታውቂ እወቂበት” አላትና ሄደ፡፡
ጥንቸል እየተዘዋወረች ቅጠል መበጠሷን ትቀጥላለች፡፡ ጥቂት እንደሄደች ዝንጀሮ እንደፈራው አንድ በቅጠል የተሸፈነ ትልቅ ጉድጓድ ውስጥ ሳታስበው ትወድቃለች፡፡ ጉድጓዱ በጣም ጥልቀት ያለው በመሆኑ በጭራሽ በቀላሉ ልትወጣ የምትችልበት አይደለም፡፡ ስለዚህ አላፊ-አግዳሚውን እንዲያወጣት ለመለመን ተገደደች፡፡
“እባካችሁ አውጡኝ፡፡ እባካችሁ እርዱኝ!” እያለች መጮህ ጀመረች፡፡ ተኩላ ድምጿን ይሰማና ወደ ጉድጓዱ አፍ ይሄዳል፡፡ አጎንብሶም ወደ ጥንቸሏ ያይ ጀመር፡፡
ጥንቸልም
“አያ ተኩላ! እባክህ ዘወር በል፡፡ ይሄ ጉድጓድ ለሁለታችን አይበቃንም፡፡ አንተ ያለህበት ቦታ እንደበረሀ የሚያቃጥል አየር ነው ያለው፡፡ እዚህ ግን በጣም ነፋሻና ቅዝቅዝ ያለ አየር ነው ያለው፡፡ ለእኔ በጣም ተስማምቶኛል፡፡ ሆኖም ወደዚህ ለመውረድ ብትችልም እንኳን ቦታው አይበቃንም” አለችው፡፡ ተኩላ፤ የጥንቸሏ ንግግር በጣም አጓጓውና፤ “ልውረድስ ብል በምኔ እወርዳለሁ?” ሲል ጠየቃት፡፡
ጥንቸልም
“እዚያ ጉድጓድ አፍ አጠገብ አንድ በገመድ የታሰረ ባሊ አለልህ፡፡ ባሊው ውስጥ ገብተህ በገመዱ ተንሸራተህ መውረድ ትችላለች” አለችው፡፡
ዕውነትም አንድ ባሊ አጠገቡ እንዳለ አየ፡፡ ባሊው ወደታች ሲወርድ ጉድጓዱ ውስጥ ያለው ገመድ ጫፍ ወደላይ የሚወጣ ነው፡፡ እንደ ፑሊ የሚሰራ ገመድ ነው፡፡ ጉድጓድ ውስጥ ያለውን ጫፍ ጥንቸሏ ይዛለች፡፡
አያ ተኩላ ባሊው ውስጥ ገብቶ ቁልቁል ተምዘግዝጎ ሲወርድ ጥንቸል የገመዱን ጫፍ ይዛ ወደ ላይ መጣች፡፡
እሱ እየወረደ፣ እሷ እየወጣች መንገድ ላይ ሲተላለፉ፤ ከት ብላ እየሳቀች፤
“አየህ አያ ተኩላ፤ ህይወት ማለት እንደዚህ ናት፡፡ አንዱ ሲወርድ አንዱ ይወጣል!“ አለችው፡፡
ተኩላ መሬት ሲደርስ ጥንቸሏ ጉድጓዱ አፋፍ ወጣች!
*   *   *
አንዳንድ ሰዎች አንድ ችግር ውስጥ ሲገቡ ሌላውን እዚያ ውስጥ ነክረው እራሳቸውን ማዳን ይችሉበታል፡፡ ተታልለው እዚያ ችግር ውስጥ የሚገቡት ሞኞች የሚሳሳቱት በአልጠግብ ባይነታቸውና እጉድጓዱ ውስጥ እንኳ ያለው ነገር እንዳያመልጠኝ ብለው ሲስገበገቡ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት በርካታ ሰዎች ጉድጓድ ውስጥ ገብተው ቀርተዋል፡፡ ዞሮ ዞሮ ሁለቱም ለሀገርና ለህዝብ አይጠቅሙም፡፡ አደጋን ከሩቅ አይተው የሚያስጠነቅቁ እንደ ዝንጀሮው ያሉ አስተዋዮች ቢኖሩም እህ ብሎ የሚያዳምጣቸው ሰው አያገኙም፡፡ ባንዱ እግር ሌላው እየገባ፣ ህይወት ትቀጥላለች፡፡
ማይ ግሪንፊልድ የተባለ ፀሐፊ፤
“ታሪክ ራሱን ይደግማል፤ ይላል ታሪከኛ ሁሉ
እኔን ያሳሰበኝ ግና፣
ታሪክ በደገመ ቁጥር፣ ዋጋው ይብስ መቀጠሉ” ይላል፡፡ የሚያስከፍለን ዋጋ እየባሰ የሚመጣው እኛ ከታሪክ ለመማር ባለመቻላችን ነው፡፡ የቀደመው የሰራውን ስህተት የኋለኛው ይደግመዋል - ያውም በዚያኛው እየሳቀ፣ እየተሳለቀ! “በእገሌ ጊዜ የተበደላችሁ እጃችሁን አውጡ!” እያለ፡፡ ከንቲባዎች ተቀያረዋል፡፡ አስተዳዳሪዎች ተቀያይረዋል፡፡ ሚኒስትሮች ተቀያይረዋል ወዘተ… ማንም ከማንም አይማርም፡፡ ሁሌ እኔ ከወደቀው የተሻልኩ ነኝ የሚለውን ለማረጋገጥ የቀደመውን እየረገሙ መቀጠል ነው!! በዚህ ዓይነት ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት እመሰርታለሁ ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ ከተነሳው ሹም መውሰድ ያለብንን ደግ ነገር ካላወቅን ከዜሮ እንደ መጀመር የከበደ ነው ጉዟችን፡፡
በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ወቅት ጀርመኖች ለንደንን በቦምብ በደበደቡ ጊዜ ሦስት ዓይነት ህዝቦች ተፈጥረው ነበር ይባላል፡፡ 1) የተገደሉ 2) ለጥቂት የተሳቱና 3) በርቀት የተሳቱ፡፡ የተገደሉት ሟቾች ናቸውና ስለአደጋው ወሬ አይነዙም፡፡ ለጥቂት የተሳቱት በሰቀቀንና ስቃዩን በማስታወስ የሚኖሩ ሆኑ፡፡ በሩቅ የተሳቱት ግን ቦምብ ጣይ አውሮፕላኖቹን ለመዷቸውና ልበ ሙሉ ሰዎች ሆኑ፤ ይለናል ፀሐፊው ማልኮልም ግላድዌል፡፡ ችግርን መልመድ ደፋርና ልበ - ሙሉ ያደርጋል ነው ነገሩ! ከዚህ ተነስቶ ለአገርና ህዝብ መቆርቆር መቻል መታደል ነው፡፡ በዚህ ወቅት ደሞ ማየት፣ በትክክለኛው ቦታ መገኘትና የሚሰሩትን በቅጡ ማወቅ ግዴታ ነው፡፡ ችግርን ለምዶ መተኛት ግን ሌላ ችግር ነው! ሁሉ በጄ ሁሉ በደጄ እያሉ አግባብነት ያለው ተግባር የማይፈፅሙ አያሌ ናቸው፡፡ የተማሩትና የሰለጠኑበት ሌላ የሚሰሩት ሌላ፤ የሆኑም አያሌ ናቸው! ስለግንባታ እያወሩ የማይገነቡ ከአፈረሰ አንድ ናቸው፡፡ መንገድ ሰርቶ በቅጡ ሳንሄድበትና ሳናጣጥመው ከፈረሰ ወይ ሰሪው በቅጡ አላበጀውም፣ ወይ ሂያጆቹ መሄድ አይችሉም፣ አሊያም ሆነ ብለው የሚያጠፉ አሉ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ በቅጡ ራስን መመርመር ያስፈልጋል፡፡ “የነቶሎ ቶሎ ቤት ግድግዳው ሰንበሌጥ”ንም ልብ ማለት መልካም ነው፡፡ ሁሉን በውል በውሉ ካላስቀመጥንና ታማኝነትን ብቻ መለኪያ እናድርግ ካልን የተወዛገበ አካሄድ ውስጥ እንሰረነቃለን፡፡ እመጫት እንደ በዛው ፅሁፍ ከዋናው ማረሚያው ይበረክታል፡፡ ከተቃወምንም ዕድሉን ባግባቡ እንጠቀም፡፡ እንዳያማህ ጥራውንም እንተው! በእጃችን ያለውን በወጉ መጠቀም ያስፈልጋል በሁሉም ወገን፡፡ አለበለዚያ “ለማይስቅ ውሻ ነጭ ጥርስ፣ ለማይገላምጥ ዶሮ፣ ቀይ ዐይን ይሰጠዋል” የሚለው የወላይተኛ ተረት ይመጣል፡፡ “ቆሎ ለዘር፤ እንዶድ ለድግር አይሆንም” እንደሚባለው ማለት ነው፡፡