Administrator

Administrator

  “አዝማሪና ውሃ ሙላት” በተሰኘው የደራሲ ከበደ ሚካኤል ግጥም ውስጥ የምናቃቸው ዝነኛ መስመሮች ለዛሬ የመረጥናቸው ናቸው፡፡

        አዝማሪና ውሃ ሙላት
        አንድ ቀን አንድ ሰው ሲሄድ በመንገድ
        የወንዝ ውሃ ሞልቶ
                ደፍርሶ ሲወርድ
        እዚያው እወንዙ ዳር
                እያለ ጐርደድ
        አንድ አዝማሪ አገኘ
                ሲዘፍን አምርሮ
        በሚያሳዝን ዜማ
            ድምፁን አሳምሮ፡፡
        “ምነው አቶ አዝማሪ
        ምን ትሠራለህ?”
        ብሎ ቢጠይቀው፤
        “ምን ሁን ትላለህ፣
        አላሻግር ብሎኝ
        የውሃ ሙላት
        እያሞጋገስኩት
        በግጥም ብዛት
        ሆዱን አራርቶልኝ ቢያሻግረኝ ብዬ”
        “አሁን ገና ሞኝ ሆንክ ምነዋ ሰውዬ
        ነገሩስ ባልከፋ
        ውሃውን ማወደስ
        ግን እንደዚህ ፈጥኖ
        በችኮላ ሲፈስ
        ምን ይሰማኝ ብለህ
        ትደክማለህ ከቶ
        ድምፁን እያሽካካ መገስገሱን ትቶ
        እስኪ ተመልከተው ይህ አወራረድ
        ያልሰማው ሲመጣ የሰማው ሲሄድ”

        ተግሳጽም ለፀባይ ካልሆነው አራሚ
        መናገር ከንቱ ነው ካልተገኘ ሰሚ!
*   *   *
በተደጋጋሚ ሀገራችን ባለፈችበት የለውጥ ሂደት ውስጥ የተገነዘብነው ዋና ነገር ገዢው “ያቀድኩትን ልተግብርበት እረፉ”፤ ሲል፤ ተገዢው “ኧረ ይሄ ነገር አልተሟላልኝም እያለ ሲያማርር፤ በመሀል ውዱ ጊዜ ማለፉ ነው፡፡ የጠፋው ጊዜ ከሰነበትን በኋላ ተመልሶ መፀፀቻችን ይሆናል፡፡ የተወሳሰበው ችግር መፍትሄ ማግኘት ቀርቶ የባሰ የተወሳሰበ ሆኖ ይገኛል፡፡ የባሰ ምስቅልቅሉ ይወጣል፡፡ መፍትሄ መስጠት ያለባቸው አካላት የውስጥም የውጪም ግፊትና ውጥረት ስላለባቸው፤ ሌሎች ችግሮችን ማስተናገድ አልሆነላቸውም። ቢወተወቱ አያዳምጡም፡፡ “አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይነቃም” የሚለው ተረት የበለጠ ይገልፀዋል፡፡ ለማደግም ሆነ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችለው መደማመጥ ነው። ሁሉንም ነገር ዐይኔን ግንባር ያድርገው ብለን አንችለውም፡፡ ካለመደማመጥ በተጨማሪ የሚደረገውንም ሆነ የተደረገውን አላውቅም፤ ማለትና መስማትም ማየትም እምቢ ካልን፣ ጉዟችን የዕውር የድንብር ይሆናል፡፡
ጊዜ እየረፈደ ከመጣ በኋላ ሁኔታውን ለመቀልበስ ብንሞክር ፍሬ-አልባ ሙከራ ይሆናል። ዛሬም ዐይናችንን ከፍተን ቆም ብለን እናስብ፡፡ ውጥረት ውስጥ ከመግባታችን በፊት የውጥረቱን መፈጠሪያ ቧንቧዎች እንዝጋ፡፡ አሁንም ደግመን ደጋግመን እናዳምጥ። ሀገራችን ከእንግዲህ ተጨማሪ ችግር የምትሸከምበት ጫንቃ የላትም፡፡ ካልተጠነቀቅን ሀገርም እንደ ሰው ተሰባሪ ናት፡፡ የ1966ን አብዮት አንርሳ፡፡ ገዢዎች መግዛት ሲያቅታቸው፣ ተገዢዎች አንገዛም ሲሉ፣ ሀገር ለአብዮት የበሰለ ሁኔታ ላይ እንደደረሰች አንዘንጋ፡፡ ሲመሽ ጉሮሮ ለጉሮሮ ከመተናነቅ፣ ፊት ለፊት ተገናኝቶ መነጋገር ነው፤ ወደ መፍትሄው የሚያስጠጋን። እስከ መቼ “ዴሞክራሲያችን ለጋ ስለሆነ ነው” እያልን ምክንያት እንሰማለን? እስከ መቼ “የመልካም አስተዳደር ችግር ነው” እያልን እንዘልቀዋለን? እስከ መቼስ “የፍትህ ሰጪ አካላት የአፈፃፀም ችግር አለ” እያልን እንጓዛለን? የድህነት ችግርስ እስከመቼ ነው ቁልፍ ነው እየተባለ የምንቀጥለው? ከሃያ በላይ ዓመታት ተጉዘን፣ ምንም ለውጥ አለማምጣታችን፣ የሚያሳፍረን ጊዜ አይመጣምን? ዛሬም መብራት ይጠፋል፡፡ ዛሬም ውሃ ይጠፋል፡፡ ዛሬም ኔትዎርክ ይቸግራል፡፡ ዛሬም ኑሮ አዘቅት ውስጥ እየከተተን ነው፡፡ እነዚህ የብሶትና የምሬት ምንጮች እስከ መቼ እንደተጫኑብን ይኖራሉ? እናስብ! ምንጣፉ ከእግራችን ስር ተስቦ እስኪወሰድ አንጠብቅ! “ጉልቻ ቢለዋወጥ ወጥ አያጣፍጥም” ከአርባ ዓመት በኋላ መድገም አሳፋሪ ይሆናል፡፡ “ፋታ ስጡኝ”  ለማለትም ጊዜ የለም! የነካነው ሁሉ ወርቅ ይሆናል ብለን እንደ ሚዳስ አስማት (Midas Touch) የምናስብበት ጊዜ አልፏል፡፡
“እስቲ ተመልከተው ይህ አወራረድ
ያልሰማው ሲመጣ የሰማው ሲሄድ”
የሚለውን ዛሬም ማስተዋል ይበጃል፡፡ መልካም ጊዜ ይመጣ ዘንድ ሁላችንም እንመኛለን!   

የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ አለመሻሻል
የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ መሻሻል ከማሳየት ይልቅ የበለጠ እየተበላሸ መጥቷል፡፡ የዚህ ምክንያት ደግሞ ለረጅም ጊዜ ችግሮች ተገቢውንና ቀጣይነት ያለው መልስ ያለማግኘታቸው ያመጣው ድምር ውጤት ነው፡፡ ማህበረሰቡ በተለያየ መንገድ ፖለቲካዊ ጥያቄዎች ነበሩት፡፡ ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎችም አሉት፡፡ ለነዚህ ጥያቄዎች ደግሞ አፋጣኝ መልስ ያለማግኘት፣ ትኩረት ማጣት፣ በቂ ክትትል አለመኖር አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የሚነሱ ጥያቄዎች እርባና ቢስ እንደሆኑ ተደርጐ መቆጠሩ ማህበረሰቡ መጨረሻ ላይ በራሱ መንገድ መፍትሄ እንዲፈልግ ነው ያስገደደው፡፡ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ መገለጫው፣ ማህበረሰቡ በዚህ መልኩ የራሱን ጥያቄ አንግቦ ጐዳና ወጥቶ፣ መንግሥትን በቀጥታ መታገል ሳይገባው፣ በወኪሎቹ በኩል የሚታገልበትና ጥያቄዎቹን የሚያቀርብበት መንገድ ነው፡፡ ይሄ አሁን በኢትዮጵያ እንዳይኖር ተደርጓል፡፡ በዚህ ምክንያት ተቃውሞ መሪ የለውም፡፡ የተደራጀ ጥያቄ የለውም፡፡ እንዲህ በሚሆንበት ጊዜ ደግሞ ምላሽ ለመስጠትም ሆነ ለመቆጣጠር የተወሳሰበና አስቸጋሪ ነው የሚሆነው፡፡ እያየን ያለነውም ይሄንን ነው፡፡
በሌላ በኩል መንግሥት ለችግሮቹ ምላሽ ለመስጠት እየሞከረ ያለው ጊዜያዊ መፍትሄዎችን ብቻ በማስቀመጥ ነው፡፡ አግባብ ያለው መልስ እየሰጠ አይደለም፡፡ ስር ነቀል ለውጥ አካሂዶ ጥያቄዎቹን በዘላቂነት የመመለስ ስራ አይደለም እየተከናወነ ያለው፡፡ ዝም ብሎ እግር በእግር እየተከታተለ ነው፣ ትንንሽ መልሶችን  ለመስጠት እየሞከረ ያለው፡፡ ይሄ ህዝቡን አያረካም፡፡ ማህበረሰቡ ደግሞ አሁን ተጨባጭና ቀጥተኛ ምላሽ ነው የፈለገው፡፡ በአሁኑ ወቅት ህዝቡ ዛሬውኑ መልሱን አምጣ ነው እያለ ያለው፡፡ ከዚህ በፊት ማህበረሰቡ ላሉት የፖለቲካ ጥያቄዎች ትእግስት ነበረው፤ ምክንያቱም ሀሳብን በነፃነት መግለፅ የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሰልፍ የመውጣት፣ የፕሬስ ነፃነት ጉዳይ ለአብዛኛው ህዝብ የልሂቃኑ ጥያቄ መስሎ ነበር የሚታየው፡፡ በዚህ ምክንያት ማህበረሰቡ ህይወቱን እስከ መሰዋት ሊሄድ አይችልም ነበር፡፡ አሁን ግን ነገሮች ተቀይረዋል። ሲከማቹ የቆዩት ችግሮችና ጥያቄዎች፣ አግባብ ያለው አፈታት ባለማግኘታቸው፣ ማህበረሰቡ ታግሶ ታግሶ፣ የራሱን አማራጭ ሊወስድ ችሏል፡፡ የተጠራቀሙ ጭቆናዎችና ፍረጃዎች ናቸው ለዚህ ያበቁት፡፡

ብሄር ተኮር ጥቃቶች   
ከብሄር ጉዳይ ጋር ተያይዞ የሚነሱት ውዝግቦች ለረጅም ጊዜያት ህብረተሰቡ ውስጥ ሲብላሉ የነበሩ ናቸው፡፡ አሁን ከመብላላት አልፈው ዋነኛ ችግር ሆነዋል፡፡ እውነቱን ለመናገር በዚች አገር፣ አንዱ ብሄር አንዱን እንዲያጠቃው የሚፈቅድ ማህበረሰብ ፈፅሞ የለም፡፡ በሌላ በኩል፣ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ ይሄ የብሄር ጉዳይ ያልተነሳበትና ያለመግባባት መንስኤ ያልሆነበት ጊዜ የለም፡፡ በወቅቱ አግባብ ያለው ውይይት ተደርጐ መልስ ቢሰጠው ኖሮ፣ ዛሬ ተመልሶ አይከሰትም  ነበር፡፡ ሰዎች ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው የመኖር መብታቸው፣ አስቀድሞ መተግበር ነበረበት፡፡ በወቅቱ እነዚህ ነገሮች ባለመታከማቸው ዛሬ ላይ ፈጠው ወጥተዋል፡፡ ከዚህ ችግር  ለመውጣት አሁንም ውይይት ያስፈልጋል፡፡ ሁነኛ የግጭት አፈታት ስልት መነደፍ አለበት፡፡ እርግጥ ነው ከህዝባችን ታሪክ ስንነሳ፣ የብሄር ግጭት ተፈጥሮ አያውቅም፡፡ ግጭቶች ሲኖሩም፣ ከድንበርና ከግጦሽ መሬት የባለቤትነት ጥያቄ አያልፍም፡፡ አሁን ግን ትንሽ ነገሮች የተቀየሩ ይመስላል፡፡
 ባለፉት 27 ዓመታትም አንዱ አንዱን ሲጨቁን፣ ሲበድል፣ ሲበዘብዝ እንደነበር ነው ሲተረክ የተኖረው። አንዱ አንዱን በጥርጣሬና በጥላቻ እንዲያይ ተደርጐ ነው፣ የማህበረሰቡ ቀደምት ግንኙነቶች ሲተረኩ የኖሩት፡፡ ታዲያ ከዚህ ተረክ ምን በጐ ፍሬ ነው የሚጠበቀው፡፡ ማህበረሰቡ “እገሌ ሀብትህን ሲበዘብዝ ነበር” ሲባል ነው የኖረው። በዚህ የተነሳ  አንዱ በሌላው የአገሪቱ ክፍል ሰርቶ ሲኖር፣ እንደ ሀብት በዝባዥ ነው የሚታየው። ንብረቴን ዘረፉኝ ነው፤ ብሶቱ፡፡ እንግዲህ ካለፉት ዓመታት ተረኮች ያተረፍነው ይሄንን ነው፡፡ ችግሩ የበለጠ አድማሱን ሳያሰፋና የአገሪቱን ህልውና ሳይፈታተን በጊዜ እልባት ማግኘት አለበት፡፡

የፖለቲከኞች መፈታትና ፋይዳው
እነዚህ ሰዎች ሀሳባቸውን በነፃነት በመግለፃቸውና በፖለቲካ አመለካከታቸው ምክንያት እስር ቤት የገቡ ናቸው፡፡ የእነዚህ ሰዎች መፈታት በእርግጥም ህዝቡ የበለጠ ትግሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ይረዳዋል፡፡ መንግሥት እነዚህን ሰዎች በመፍታቱ ብቻ ለህዝቡ ጥያቄ በቂ መልስ ሰጥቻለሁ ብሎ ካሰበ በእጅጉ ተሳስቷል፡፡ ምክንያቱም የእስረኞች መፈታት ጉዳይ ከህዝቡ ጥያቄዎች አንዱ እንጂ ዋነኛ ግብና ዓላማ አይደለም፡፡ እርግጥ ነው ማህበረሰቡ እንዲፈቱ ታግሎላቸዋል፡፡ ስለዚህ መፈታታቸው እንደ አንድ ድል ነው የሚቆጠረው፤ ግን የጥያቄዎች ሁሉ መልስ አይሆንም፡፡

የህግ የበላይነትና ሰብአዊ መብት
የህግ የበላይነትን ማስከበር የመንግስት ዋነኛ ሃላፊነት ነው፡፡ ጥያቄው የህግ የበላይነትን ማስከበር ሲባል በምን መንገድ የሚለው ነው፡፡ የህግ የበላይነትን በሌላ የህግ ጥሰትና ጥፋት ለማስከበር ጥረት የሚደረግ ከሆነ ውጤት አያመጣም፡፡ መንግሥት ደግሞ የህግ የበላይነትን ለማስከበር ሲጥር፣ የማህበረሰቡን የህግ ንቃተ ህሊና ማገናዘብ አለበት፡፡ መፍትሄው የህይወት ማጥፋት ሳይሆን አጥፊዎችን በህግ ጥላ ስር ማዋል ነው፡፡ የህግ የበላይነትን ለማስከበር የሚወሰደው እርምጃ የበለጠ ጥፋት የሚያስከትል ከሆነ ቆም ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ መንግሥት ችግሮችን የመፍታት አቅም ከሌለው፣ ከሚችሉ ሰዎች ጋር ህብረት ፈጥሮ መፍታት ነው የሚበጀው፡፡ እስካሁን ይሄን ማድረግ አልቻለም፡፡ ከዚህ በኋላም ይሄን ለማድረግ ጊዜ አለው፡፡ ወደ ህብረተሰቡ ቀርቦ በመነጋገር፣ ተከታታይ የመትሄ ሀሳቦችን ማመንጨትና ተግባር ላይ ማዋል ያስፈልጋል፡፡

የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ አለመሻሻል
የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ መሻሻል ከማሳየት ይልቅ የበለጠ እየተበላሸ መጥቷል፡፡ የዚህ ምክንያት ደግሞ ለረጅም ጊዜ ችግሮች ተገቢውንና ቀጣይነት ያለው መልስ ያለማግኘታቸው ያመጣው ድምር ውጤት ነው፡፡ ማህበረሰቡ በተለያየ መንገድ ፖለቲካዊ ጥያቄዎች ነበሩት፡፡ ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎችም አሉት፡፡ ለነዚህ ጥያቄዎች ደግሞ አፋጣኝ መልስ ያለማግኘት፣ ትኩረት ማጣት፣ በቂ ክትትል አለመኖር አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የሚነሱ ጥያቄዎች እርባና ቢስ እንደሆኑ ተደርጐ መቆጠሩ ማህበረሰቡ መጨረሻ ላይ በራሱ መንገድ መፍትሄ እንዲፈልግ ነው ያስገደደው፡፡ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ መገለጫው፣ ማህበረሰቡ በዚህ መልኩ የራሱን ጥያቄ አንግቦ ጐዳና ወጥቶ፣ መንግሥትን በቀጥታ መታገል ሳይገባው፣ በወኪሎቹ በኩል የሚታገልበትና ጥያቄዎቹን የሚያቀርብበት መንገድ ነው፡፡ ይሄ አሁን በኢትዮጵያ እንዳይኖር ተደርጓል፡፡ በዚህ ምክንያት ተቃውሞ መሪ የለውም፡፡ የተደራጀ ጥያቄ የለውም፡፡ እንዲህ በሚሆንበት ጊዜ ደግሞ ምላሽ ለመስጠትም ሆነ ለመቆጣጠር የተወሳሰበና አስቸጋሪ ነው የሚሆነው፡፡ እያየን ያለነውም ይሄንን ነው፡፡
በሌላ በኩል መንግሥት ለችግሮቹ ምላሽ ለመስጠት እየሞከረ ያለው ጊዜያዊ መፍትሄዎችን ብቻ በማስቀመጥ ነው፡፡ አግባብ ያለው መልስ እየሰጠ አይደለም፡፡ ስር ነቀል ለውጥ አካሂዶ ጥያቄዎቹን በዘላቂነት የመመለስ ስራ አይደለም እየተከናወነ ያለው፡፡ ዝም ብሎ እግር በእግር እየተከታተለ ነው፣ ትንንሽ መልሶችን  ለመስጠት እየሞከረ ያለው፡፡ ይሄ ህዝቡን አያረካም፡፡ ማህበረሰቡ ደግሞ አሁን ተጨባጭና ቀጥተኛ ምላሽ ነው የፈለገው፡፡ በአሁኑ ወቅት ህዝቡ ዛሬውኑ መልሱን አምጣ ነው እያለ ያለው፡፡ ከዚህ በፊት ማህበረሰቡ ላሉት የፖለቲካ ጥያቄዎች ትእግስት ነበረው፤ ምክንያቱም ሀሳብን በነፃነት መግለፅ የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሰልፍ የመውጣት፣ የፕሬስ ነፃነት ጉዳይ ለአብዛኛው ህዝብ የልሂቃኑ ጥያቄ መስሎ ነበር የሚታየው፡፡ በዚህ ምክንያት ማህበረሰቡ ህይወቱን እስከ መሰዋት ሊሄድ አይችልም ነበር፡፡ አሁን ግን ነገሮች ተቀይረዋል። ሲከማቹ የቆዩት ችግሮችና ጥያቄዎች፣ አግባብ ያለው አፈታት ባለማግኘታቸው፣ ማህበረሰቡ ታግሶ ታግሶ፣ የራሱን አማራጭ ሊወስድ ችሏል፡፡ የተጠራቀሙ ጭቆናዎችና ፍረጃዎች ናቸው ለዚህ ያበቁት፡፡

ብሄር ተኮር ጥቃቶች   
ከብሄር ጉዳይ ጋር ተያይዞ የሚነሱት ውዝግቦች ለረጅም ጊዜያት ህብረተሰቡ ውስጥ ሲብላሉ የነበሩ ናቸው፡፡ አሁን ከመብላላት አልፈው ዋነኛ ችግር ሆነዋል፡፡ እውነቱን ለመናገር በዚች አገር፣ አንዱ ብሄር አንዱን እንዲያጠቃው የሚፈቅድ ማህበረሰብ ፈፅሞ የለም፡፡ በሌላ በኩል፣ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ ይሄ የብሄር ጉዳይ ያልተነሳበትና ያለመግባባት መንስኤ ያልሆነበት ጊዜ የለም፡፡ በወቅቱ አግባብ ያለው ውይይት ተደርጐ መልስ ቢሰጠው ኖሮ፣ ዛሬ ተመልሶ አይከሰትም  ነበር፡፡ ሰዎች ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው የመኖር መብታቸው፣ አስቀድሞ መተግበር ነበረበት፡፡ በወቅቱ እነዚህ ነገሮች ባለመታከማቸው ዛሬ ላይ ፈጠው ወጥተዋል፡፡ ከዚህ ችግር  ለመውጣት አሁንም ውይይት ያስፈልጋል፡፡ ሁነኛ የግጭት አፈታት ስልት መነደፍ አለበት፡፡ እርግጥ ነው ከህዝባችን ታሪክ ስንነሳ፣ የብሄር ግጭት ተፈጥሮ አያውቅም፡፡ ግጭቶች ሲኖሩም፣ ከድንበርና ከግጦሽ መሬት የባለቤትነት ጥያቄ አያልፍም፡፡ አሁን ግን ትንሽ ነገሮች የተቀየሩ ይመስላል፡፡
 ባለፉት 27 ዓመታትም አንዱ አንዱን ሲጨቁን፣ ሲበድል፣ ሲበዘብዝ እንደነበር ነው ሲተረክ የተኖረው። አንዱ አንዱን በጥርጣሬና በጥላቻ እንዲያይ ተደርጐ ነው፣ የማህበረሰቡ ቀደምት ግንኙነቶች ሲተረኩ የኖሩት፡፡ ታዲያ ከዚህ ተረክ ምን በጐ ፍሬ ነው የሚጠበቀው፡፡ ማህበረሰቡ “እገሌ ሀብትህን ሲበዘብዝ ነበር” ሲባል ነው የኖረው። በዚህ የተነሳ  አንዱ በሌላው የአገሪቱ ክፍል ሰርቶ ሲኖር፣ እንደ ሀብት በዝባዥ ነው የሚታየው። ንብረቴን ዘረፉኝ ነው፤ ብሶቱ፡፡ እንግዲህ ካለፉት ዓመታት ተረኮች ያተረፍነው ይሄንን ነው፡፡ ችግሩ የበለጠ አድማሱን ሳያሰፋና የአገሪቱን ህልውና ሳይፈታተን በጊዜ እልባት ማግኘት አለበት፡፡

የፖለቲከኞች መፈታትና ፋይዳው
እነዚህ ሰዎች ሀሳባቸውን በነፃነት በመግለፃቸውና በፖለቲካ አመለካከታቸው ምክንያት እስር ቤት የገቡ ናቸው፡፡ የእነዚህ ሰዎች መፈታት በእርግጥም ህዝቡ የበለጠ ትግሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ይረዳዋል፡፡ መንግሥት እነዚህን ሰዎች በመፍታቱ ብቻ ለህዝቡ ጥያቄ በቂ መልስ ሰጥቻለሁ ብሎ ካሰበ በእጅጉ ተሳስቷል፡፡ ምክንያቱም የእስረኞች መፈታት ጉዳይ ከህዝቡ ጥያቄዎች አንዱ እንጂ ዋነኛ ግብና ዓላማ አይደለም፡፡ እርግጥ ነው ማህበረሰቡ እንዲፈቱ ታግሎላቸዋል፡፡ ስለዚህ መፈታታቸው እንደ አንድ ድል ነው የሚቆጠረው፤ ግን የጥያቄዎች ሁሉ መልስ አይሆንም፡፡

የህግ የበላይነትና ሰብአዊ መብት
የህግ የበላይነትን ማስከበር የመንግስት ዋነኛ ሃላፊነት ነው፡፡ ጥያቄው የህግ የበላይነትን ማስከበር ሲባል በምን መንገድ የሚለው ነው፡፡ የህግ የበላይነትን በሌላ የህግ ጥሰትና ጥፋት ለማስከበር ጥረት የሚደረግ ከሆነ ውጤት አያመጣም፡፡ መንግሥት ደግሞ የህግ የበላይነትን ለማስከበር ሲጥር፣ የማህበረሰቡን የህግ ንቃተ ህሊና ማገናዘብ አለበት፡፡ መፍትሄው የህይወት ማጥፋት ሳይሆን አጥፊዎችን በህግ ጥላ ስር ማዋል ነው፡፡ የህግ የበላይነትን ለማስከበር የሚወሰደው እርምጃ የበለጠ ጥፋት የሚያስከትል ከሆነ ቆም ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ መንግሥት ችግሮችን የመፍታት አቅም ከሌለው፣ ከሚችሉ ሰዎች ጋር ህብረት ፈጥሮ መፍታት ነው የሚበጀው፡፡ እስካሁን ይሄን ማድረግ አልቻለም፡፡ ከዚህ በኋላም ይሄን ለማድረግ ጊዜ አለው፡፡ ወደ ህብረተሰቡ ቀርቦ በመነጋገር፣ ተከታታይ የመትሄ ሀሳቦችን ማመንጨትና ተግባር ላይ ማዋል ያስፈልጋል፡፡

 119 እስረኞች ክሳቸው ተቋረጠ ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ፣ ብርጋዴል ጀነራል ተፈራ ማሞና ብርጋዴል ጀነራል አሳምነው ፅጌ ይገኙበታል

     የሚኒስትሮች ም/ቤት ከትላንትናው እለት ጀምሮ የሚፀና የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ያወጀ ሲሆን ለ6 ወራት እንደሚቆይ ተገልጿል፡፡
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የታወጀው በህዝባዊ አመፅና አድማ፣ የመንግሥትና የግል ንብረቶች ውድመትና የሰው ህይወት መጥፋትን ለማስቀረት ነው ተብሏል፡፡ አዋጁ ከ15 ቀናት በኋላ ለህዝብ ተወካዮች ም/ቤት ቀርቦ እንደሚፀድቅ ታውቋል፡፡
በሌላ በኩል 119 እስረኞች በትላንትናው እለት ክሳቸው የተቋረጠ ሲሆን 56 የግንቦት 7 አባላት ተብለው የተጠረጠሩ እንዲሁም 41 የኦነግ አባላት ተብለው የተጠረጠሩ መሆናቸው ታውቋል፡፡
ክሳቸው እንዲቋረጥ ከተደረጉት መካከል ኮ/ል ደመቀ ዘውዱ፣ ብርጋዴል ጀነራል ተፈራ ማሞና ብርጋዴል ጀነራል አሳምነው ፅጌ ይገኙበታል፡፡

 የፊፋ ዓለም ዋንጫው ከ50 በላይ ሀገራትን ሲያካልል ወደ ኢትዮጵያ በታሪክ ለሁለተኛ ጊዜ በኮካ ኮላ ኩባንያ አማካኝነት መምጣቱ ለስፖርት አፍቃሪው ትልቅ ክብር ነው፡፡ የታላቁ የስፖርት መድረክ አካል የመሆን እድልን ይፈጥራል፡፡ ለአሸናፊ የሚበረከት ዋንጫ በቅርበት ለማየት መቻል በህይወት አንዴ የሚመጣ እድል ነው።   በኢትዮጵና በአፍሪካ ቀንድ የኮካ ኮላ ብራንድ ማናጀር የሆኑት ወ/ት ትዕግስት ጌቱ “የዓለም ዋንጫውን ወደ ኢትዮጵያ ለሁለተኛ ጊዜ ማምጣት በመቻላችን ትልቅ ኩራት ይሰማናል ብለው የኢትዮጵያ ህዝብ ለእግር ኳስ ስፖርት ላለው የማይሞት ፍቅር የሰጠነውን እውቅናና ክብር የሚያሳይ ነው” በማለት ተናግረዋል፡፡ “እግር ኳስ በባህል፣ በሀይማኖት እና ፖለቲካ ሳይገደብ ህዝቦችን አንድ የማድረግ ሀይል አለው፡፡ ኮካ ኮላ ይህንን የፊፋን አለም ዋንጫ የመመልከት የተለየ አጋጣሚ ለኢትዮጵያውን መፍጠሩ ትልቅ ስኬት ነውም” ብለዋል፡፡ ኮካ ኮላ በዓለም ግዙፉ የመጠጥ ካምፓኒ ሲሆን ወደ 500 የሚደርሱ የተለያዩ የመጠጥ ብራንዶችን ከ200 ሀገራተ በላይ ለሚገኙ ለደንበኞቹ ያደርሳል፡፡ ከሁለት መቶ በላይ የሆኑ ሀገራት የሚገኙ ተጠቃሚዎቻችንን በቀን በ1.7 ቢሊዮን መስተንግዶዎች በማዝናናት ላይ ይገኛል፡፡
ኢስት አፍሪካን ቦትሊንግ ሊሚትድ ከኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽንና ከወጣቶችና ስፖርት ሚኒስቴር በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ስለ ዓለም ዋንጫ የኢትዮጵያ ጉብኝት መግለጫ ሰጥተው ነበር፡፡ ኢትዮጵያውያን የእግረ ኳስ አፍቃሪዎች ተወዳጁ ዋንጫ ወደ ሀገሪቱ በሚመጣ ወቅት ለመመልከት የሚችሉባቸውን የለተያዩ እድሎች ያመለከተ መግለጫ ነበር፡፡ በመጀመሪያ ከሱዳን ቆይታው በኋላ ዋንጫው ወደ ኢትዮጵያ የካቲት 17 ቅዳሜ ጠዋት ሲደርስ አዲስ አበባ ኤርፖርት ታላላቅ ባለስልጣናት፣ ሚኒስትሮች እና የኮካ ኮላ ኩባንያ በኢትዮጵያ ሀላፊዎች በተገኙበት የደመቀ አቀባበል ይደረግለታል፡፡ በመቀጠልም በብሄራዊ ቤተመንግስት የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ዋንጫውን የሚረከቡት ስነ ስርዐት የሚከናወን ሲሆን፣ ከቤተ መንግስት ቆይታው በመቀጠል የዓለም ዋንጫው ለጋዜጣዊ መግለጫ ወደ ሂልተን ሆቴል የሚያመራ ይሆናል፡፡ ከጋዜጣዊ መግለጫው በኋላ የፎቶ ፕሮግራም የሚኖር ሲሆን፣ በዚህ ስነ ሰርዐትም ጋዜጠኞች ከዋንጫው ጋር የማስታወሻ ፎቶ መነሳት የሚችሉበት አጋጣሚ ተፈጥሮላቸዋል፡፡ በሁለተኛ ቀን እሁድ፣ የካቲት 18፤ 2010 ዓ.ም የፊፋ አለም ዋንጫ የኢትዮጵያ ቆይታ መላው የስፖርተ አፍቃሪ ህዝብ ከፊፋ የአለም ዋንጫ ጋር የማይረሳ ቀን የሚያሳልፉበት አስደሳችና አዝናኝ ውሎ በግዮን ሆቴል ይካሄዳል፡፡
የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ
የዓለም ዋንጫ በፊፋ ዋና አዘጋጅነት በ1930 እ.ኤ.አ ላይ በደቡብ አሜሪካዋ ኡራጋይ መካሄድ ከመጀመሩ ሁለት ዓመት በፊት የውድድሩ  ደንብ ሲቀረፅ ለአሸናፊ ለየት ያለ የክብር ዋንጫ እንዲሸለም ውሳኔ ላይ ተደረሰ፡፡  ይህንኑ የዋንጫ ሽልማት በጥሩ ዲዛይን እንዲሰራ ታላቁና ከባዱ ታሪካዊ ኃላፊነት ለፈረንሳዊው ቀራፂ አቤል ላፍሌዌር ተሰጠው፡፡ ፈረንሳዊው ቀራፂም የተሰጠውን የታሪክ አደራ ባግባቡ በመወጣት አስደናቂዋን ዋንጫ አዘጋጅቶ ሊያቀርብ ቻለ፡፡ የፊፋ ፕሬዚዳንት ለነበሩት ፈረንሳዊው ጁሊየስ ሪሜት መታሰቢያ ሆና ‹የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ› ተባለች፡፡
የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ ለዓለም ዋንጫ አሸናፊዎች ከ1ኛው የዓለም ዋንጫ አንስቶ መሸለም ከጀመረች በኋላ የተለያዩ ታሪካዊ ክስተቶች ተፈራርቀውባታል፡፡ 1ኛው የዓለም ዋንጫ በኡራጓይ በ1930 እ.ኤ.አ ላይ ተካሂዶ ተጀምሮ እስከ 1938 እ.ኤ.አ በፈረንሳይ እስከ ተዘጋጀው 3ኛው የዓለም ዋንጫ ሶስተኛው ሻምፒዮና ከዘለቀ በኋላ 2ኛው የዓለም ጦርነት ፈነዳ፡፡  በዚያ ወቅት የፊፋ ም/ፕሬዚዳንት የነበሩት ጣሊያናዊው ዶ/ር አሪኖ ባራሲ ውድድሩ በተቋረጠባቸው 12 ዓመታት የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ በኃላፊነታቸው ስር ሆና በአደራ ያስቀመጧት ነበረች፡፡ ጣልያናዊው የዓለም ዋንጫዋን ከሁለተኛው ዓለም ጦርነት ወራሪ ኃይሎች ዘረፋ ለመጠበቅ ሲሉ በጫማ ሳጥን ውስጥ አኑረዋታል፡፡ በአንድ አጋጣሚ በቤታቸው ፋሽቶች ፍተሻ ሲያደርጉ አልጋ ስር በመደበቅም አትርፈዋታል፡፡
በ1966 እ.ኤ.አ ላይ ደግሞ የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ በጊዜው የውድድር አዘጋጅ በነበረችው እንግሊዝ ያጋጠማት አስደንጋጭ ታሪክም ነበር፡፡ ለዓለም ዋንጫው መስተንግዶ ማሟሟቂያ ይሆናል ተብሎ የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ ለጉብኝት ቀርባ ከነበረችበት የኤግዚቢሽን ማዕከል በመጥፋቷም ነበር፡፡ ያን ጊዜ የዋንጫዋ መጥፋትና መሰረቅ ከታወቀ በኋላ  በዋናው የውድድር መድረክ ላይ አለመረጋጋት እንደሚፈጥር ስጋት ሆኖ ነበር፡፡ ባልተጠበቀ ሁኔታ ግን ለኤግዚቢሽን ቀርባ ከነበረችበት ግዙፍ ህንፃ ብዙም ሳይርቅ የሚገኝ ትልቅ ዛፍ ስር መሬት ውስጥ በጋዜጣ ተጠቅልላ እንደተቀበረች ተገኘች። ለሕዝብ እይታ ቀርባ ከነበረችበት ስፍራ የጠፋችው ባልታወቁ ሌቦች ተሰርቃ ነበር፡፡ አንዲት ብልህ ውሻ ግን ከጌታዋ ጋር ስትንሸራሸር ዛፍ ስር የሚገኘውን መሬት ምሳ የተቀበረችውን ዋንጫ አግኝታለች፡፡ ለእንግሊዝና ለእግር ኳሱ አለም ታላቅ ውለታን ያደረገችው ውሻዋ ፒክልስ ትባል ነበር፡፡
በ1970 እ.ኤ.አ በሜክሲኮ ተደርጎ እስከ ነበረው 8ኛው የዓለም ዋንጫ የዓለም ሻምፒዮናነቱን ብራዚል ለሶስተኛ ጊዜ በማሸነፏ የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ የዘላለም ንብረት አድርጋት ነበር፡፡ የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ ላንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በታላቁ የስፖርት መድረክ ህልውናዋ ያበቃው በ1983 እ.ኤ.አ ላይ በብራዚል ዋና ከተማ ሪዩዲጂኔሮ በዘራፊ ወሮበሎች ከተሰረቀች በኋላ ነበር። በወቅቱ ዋንጫዋን የሰረቁት ወሮበሎች ሌብነታቸው እንዳይነቃ  በማለት የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫን በፍም እሳት አቀለጧት እናም ወደ ሌላ ቅርፅ እንደቀየሯት በመላው ዓለም ተወስቶ ነበር፡፡ ብራዚል በዚህ ዘመን ዋንጫዋን ለሶስት ጊዜ ለማሸነፍ በመቻሏ ለዘላለም ማስቀረት የምትችላትን ኦርጅናል የጁሊዬስ ሪሜት ዋንጫ ማጣቷ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ፊፋን ያስደነገጠ ታሪካዊ ክስተት ነበር፡፡ የብራዚል ወሮበሎች የታሪክ ሌብነት የብራዚልን የዓለም ዋንጫ ስኬት ያሰናከለው ቢመስልም፤ በወቅቱ የነበረው የሀገሪቱ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለፊፋ ባቀረበው ጥያቄ መሰረት ተመሳሳይ የጁሊየስ ሩሜት ዋንጫ እንዲሰራ ተደርጎ ምትኳ የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ ለብራዚል ብሄራዊ ቡድን ተበርክቷል፡፡
ኦሪጅናሏ የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ በመጠኗ አነስተኛ ነች፡፡ 35 ሴ.ሜ ቁመት ያላት ስትሆን እስከ 3.8 ኪ.ግ. የክብደት መጠን ነበራት፡፡ የዋንጫዋ አብዛኛው ክፍል የተቀረፀው በጠራ የብር ማዕድን ሲሆን ዙሪያዋን በተወሰነ የወርቅ ለምድ የተለበጠች ነበረች፡፡ የዋንጫዋ መሰረት ሰማያዊ ቀለም የነበረው ሲሆን በከፊል የከበረ ድንጋይ Lapis Lazuic  ከተባለ ማዕድን የተሰራ ነው፡፡ በዋንጫዋ ታችኛው ክፍል ያሉት አራት ጎኖች ዙሪያቸውን በወርቅ የተለበጡ ሲሆን ስፍራው የአሸናፊዎች ዝርዝር እንዲሰፍርበት የተዘጋጀ ነበር፡፡ ዓለም ዋንጫ በጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ ሽልማትነት ከ1930-70 እ.ኤ.አ የተካሄደች ሲሆን በዋንጫዋ ታችኛው ክፍል በሚገነው በዚሁ የወርቅ ለምድ ላይ በእነዚያ ጊዜያት በውድድሩ ሻምፒዮን ለመሆን የበቁ ዘጠኝ ሀገራት ብሔራዊ ቡድኖችም ስም ተቀርጾ ሰፍሮበታል፡፡  ብራዚል በ1958, 1962, 1970፣ ኡራጋይ በ1930, 1950፣ ጣሊያን በ1934, 1938፣ ምዕራብ ጀርመን በ1954 እና እንግሊዝ በ1966 እ.ኤ.አ የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫን አሸንፈዋል፡፡
አዲሷ የፊፋ ዓለም ዋንጫ
አዲሷ የፊፋ የዓለም ዋንጫ በ1970 እ.ኤ.አ ላይ ሜክሲኮ ባዘጋጀችው 9ኛው የዓለም ዋንጫ ብራዚል የዓለም ሻምፒዮናነቱን ለሶስተኛ ጊዜ ማሸነፍ በመቻሏ የጁሊየስ ሪሜት ዋንጫ የዘላለም ንብረቷ በማድረግ ከሰረቀች በኋላ የተፈጠረች ናት፡፡ ፊፋ የውድድሩን አዲስ የዋንጫ ሽልማት ለማዘጋጀት ውሳኔ ከላይ ከደረሰ በኋላ፤ የዓለም ዋንጫን ሽልማት በመቅረፅ ከ7 ሀገራት የተውጣጡ ቀራፂዎች የሰሯቸው 53 የተለያዩ ዲዛይኖች ለውድድር ቀርበዋል፡፡ በመጨረሻም የፊፋ ኮንግረስ ባሳለፈው ውሳኔ የጣሊያኑን ቀራፂ ሲልቪዮ ጋዚንጋን የዋንጫ ቅርፅና የስራ ሃሳብ ተቀባይነት አገኘ፡፡ በዚህ መሠረት በ1974 እ.ኤ.አ በተከናወነው 10ኛው የዓለም ዋንጫ ላይ ፊፋ አዲሷንና ዛሬ ድረስ የዘለቀችውን የዓለም ዋንጫ ለታላቋ የስፖርት መድረክ ለማቅረብ በቃ፡፡  አዲሲቷ የፊፋ የዓለም ዋንጫ የዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ንብረት ሆኖ ለዘላለም የምትቆይ ናት፡፡ ፊፋ በመተዳደሪያ ደንቡ እንደሚያመለክተው ዋንጫዋን ያሸነፈ ብሔራዊ ቡድን ሙሉ በሙሉ በወርቅ የተሰራችውን ሽልማት ለተወሰኑ የፌሽታ ሰሞናት ጠብቆ እንዲያቆይ ቢፈቀድለትም ኦርጅናሌዋን ዋንጫ አስረክቦ በፊፋ የተዘጋጀውን ተመሳሳይ ዋንጫ እንዲወስድ ይደረጋል፡፡ አዲሷ የዓለም ዋንጫ ሽልማት ዛሬም ድረስ ከውድድሩ ጋር አብራ እንደቆየች ትገኛለች፡፡ የዓለም ዋንጫዋ 36 ሴ.ሜ ርዝማኔ ሲኖራት የተሰራችው 4 ሺህ 970 ግራም ክብደት ከሚመዝን 18 ካራት ንፁህ ወርቅ ነው፡፡ የዋንጫዋ የታችኛው ክፍል በከፊል የከበረ ድንጋይ ከሆነው ማልቺይት ከተባለ ማዕድን የተለበጠና የተዘጋጀ ነው፡፡ በዚሁ የዋንጫው ክፍል ላይ በ2014 እኤአ እስከተከናወነው 20ኛው ዓለም ዋንጫ ድረስ በሻምፒዮናነት ታሪክ የሰሩ አገራት ተቀርፀው ሰፍረውበታል፡፡ የዓለም ሻምፒዮናዎቹ ዝርዝር የሚፃፍበት ይኸው ቦታው እስከ 2030 እ.ኤ.አ ለሚያሸንፉ ብሔራዊ ቡድኖች ቦታ እንዳለው ቢታወቅ የዓለም ዋንጫ 100ኛ ዓመት ሲከበር አዲስ ዲዛይን ሊሰራ እንደሚችል ይጠበቃል፡፡
የአሁኗን ዋንጫ ለመጀመሪያ ጊዜ  በድል ሊስማት የቻለው የጀርመን ብሔራዊ ቡድን አምበል ፍራንዝ ቤከን ባወር ነበር፡፡ በ1974 እ.ኤ.አ በተካሄደው በዚህ ዓለም ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታ የተደረገው በሆላንድና በአዘጋጇ ምዕራብ ጀርመን መካከል ነበር፡፡ ጀርመንም ይህችኑ ዓለም ለመጀመርያ ጊዜ ያሸነፈች የአውሮፓ አገር ሆናለች፡፡ በ1978 እ.ኤአ ላይ ደግሞ በሞናሞናታል ስታድዬም ቦነስ አይረስ ከተማ ላይ ይህችኑ ዓለም ዋንጫ አርጀንቲና ተቀዳጅታ የመጀመሪያዋ ደቡብ አሜሪካ ሀገር ለመሆን በቅታለች፡፡
ጣሊያናዊው ቀራፂ ሲሊቪዮ ጋዚንጋ የሰሯት የፊፋ ዓለም ዋንጫ በታሪኳ በርካታ የዓለማችንን ታላላቅ ከተሞችን በሻምፒዮኖቹ እና በአዘጋጆቹ አገራት አማካኝነት ጎብኝታለች፡፡ ቦነስ አየረስ፤ ሳንቲያጎ፤ ማድሪድ፤ ሮም፣ ሎስ አንጀለስ፣ ፓሪስ፣ ዮክሃማ፤ በርሊን፤ ጆሃንስበርግና ሪዮዲጄኔሮ ይገኙበታል፡፡ የዓለም ዋንጫ ሽልማት የእግር ኳስ ስፖርትን ዓለም አቀፋዊነትና ታላቅ ውበት ተምሳሌት ተደርጋ የተቀረፀች ዋንጫ መሆኗን ቀርፂዋ ሲልቪዮ ጋዚንጋ ይናገራሉ፡፡ ስለ አንዱ የዓለም ዋንጫ ትዝታቸው ሲናገሩ “ጣሊያናዊ እንደመሆኔ” ስኳድራ አዙራ የተባለውን ብሔራዊ ቡድናችንን እደግፋለሁ፡፡ ስለዚህም በ1982 እ.ኤ. በሳንቲያጎ በርናባኦ ስታድዬም ማድሪድ ከተማ ውስጥ የጣሊያን ቡድን ዋንጫውን በማንሳት የፈፀመው ገድል ምንጊዜም አልዘነጋውም፡፡ ግብ ጠባቂው ዲኖ ዞፍ በጣሊያናዊ የተሠራቸውን ይህችን ዋንጫ ሲያነሳ በጣም ኮርቻለሁ። ዓለም ዋንጫዋ በገጽታዋ ጣሊያንን ብታንፀባርቅ አይደንቅም” ብለው ነበር፡፡ ከ1974 እ.ኤ.አ ወዲህ የአሁኗን የፊፋ የዓለም ዋንጫን ሶስት ጊዜ በመውሰድ ግንባር ቀደም የሆነችው ጀርመን (በ1974 ፤ በ1990ና በ2016 እ.ኤ.አ) ላይ በማሸነፍ ነው፡፡ ሁለት እኩል ያሸነፉት ደግሞ ብራዚል (በ1994 እና በ2002 እ.ኤ.አ) ፤ (ጣሊያን በ1982 እና በ2006 እ.ኤ.አ)  እና  አርጀንቲና (በ1978 እና በ1986 እ.ኤ.አ) ላይ ሲሆን፤እንዲሁም  ፈረንሳይ በ1998ና ስፔን በ2010 እ.ኤ.አ የዓለም ዋንጫዋን እኩል አንዴ በሻምፒዮናነት አንስተዋል፡፡
የዓለም ዋንጫ ዋጋዋና የመስተንግዶ ገቢዋ
ሲልቪዮ ጋዚንጋ በ95 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩት ከዓመት በፊት ሲሆን፤ የሰሯትን የዓለም ዋንጫ እንደ ልጄ የምቆጥራት የስነ ጥበብ ውጤት ናት ብለው ነበር፡፡ በ1971 እ.ኤ.አ ላይ ዲዛይን አድርገው እንደጨረሷት የዋንጫዋ ዋጋ እስከ 50 ሺህ ዶላር ይገመት ነበር፡፡ ዘንድሮ በወቅታዊው ዋጋ የፊፋ ዓለም ዋንጫ ከ20 ሚሊዮን ዶላር በላይ እንደምታወጣ ተተምኗል። በነገራችን ላይ የዓለም ዋንጫን የሚያህል ታላቅ የስፖርት መድረክ በማዘጋጀት በአማካይ ከ5-9 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘታቸው የዋንጫዋን ውድ ስጦታነት ያመላክታል፡፡
በ2002 እ.ኤ.አ ላይ ጃፓንና ደቡብ ኮሪያ 17ኛውን የዓለም ዋንጫ በማስተናገድ 9 ቢሊዮን ዶላር፣ በ2006 እ.ኤ.አ ላይ ጀርመን 18ኛውን የዓለም ዋንጫ በማስተናገድ 12 ቢሊዮን ዶላር፤ በ2010 እ.ኤ.አ ላይ ደቡብ አፍሪካ 19ኛውን የዓለም ዋንጫ በማስተናገድ 5 ቢሊዮን ዶላር እንዲሁም በ2014 እ.ኤ.አ ብራዚል 20ኛውን የዓለም ዋንጫ በማስተናገድ  እስከ 14 ቢሊዮን ዶላር ገቢ አግኝተዋል፡፡ የዓለም ዋንጫን ለ32 አገራት አዘጋጅቶ ለአሸናፊው የሚሸልም አገር በአገሪቱ ኢኮኖሚ ላይ 30 ቢሊየን ዶላር እንዲንቀሳቀስ ያደርጋል፡፡ ዓለም ዋንጫውን በሚያዘጋጅበት 4 ዓመታት ውስጥ ደግሞ እስከ 4 ሚሊየን ለሚደርሱ ዜጎች የስራ ዕድል የሚፈጥር ይሆናል፡፡
የዓለም ዋንጫም ዋጋ እስከ 20 ሚሊዮን ዶላር መተመኑን የሚስተካከል ሌላ የስፖርት ሽልማት የለም። ከእግር ኳሱ ዓለም ውድ ዋጋ ያለው ሽልማት ተብሎ ቢጠቀስ የዓለማችን አንጋፋው የክለቦች ውድድር የሆነው የእንግሊዝ ኤፍኤ ካፕ ነው፡፡ ለ5 የተለያዩ ጊዜያት የተቀረፀው ይሄ የኤፍ ኤ ካፕ ዋንጫ እስከ 420 ሺ ፓውንድ ያወጣል፡፡ የዓለማችን ቁጥር 1 የክለቦች ውድድር የሆነው የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ዋንጫ ከ1992 እ.ኤ.አ አንስቶ ለሻምፒዮኖቹ የሚበረከት ነው፡፡ ምንም እንኳን በቴሌቪዥን ስርጭት መብት፣ በስታድየም ገቢ፣ በስፖንሰርሺፕ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ሻምፒዮን እስከ 200 ሚሊዮን ዶላር ቢያገኝም ዋንጫው ግን ያን ያህል አያወጣም፡፡ በብር ተለብጦ የተሰራው የእንግሊዝ ፕሮሚር ሊግ ዋንጫ ማልቻለት የተባለ የከበረ ማዕድን መሰረት የሆነለት ነው፡፡ 104 ሴ.ሜትሮች የሚረዝምና 25 ኪ.ግ የሚመዝን ነው፡፡ የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ የተለበጠበት ብር በዋጋ ቢተመን ከ10 ሺ ዶላር አይበልጥም፡፡ በ1967 እ.ኤ.አ ላይ የተሰራው የአውሮፓ ሻምፒየንስ ሊግ ዋንጫ 71 ሴ.ሜትር የሚረዝምና 7.5 ኪ.ግ ክብደት ያለው ሲሆን፤ በምንም አይነት ዋጋ አልተተመነም፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር ደንብ መሰረት ማንም ቀርፆ የመሸጥ መብት የለውም፡፡  

 ከ5 ሺ ብር እስከ 10 ሺ ብር ሽልማት ተዘጋጅቷል
 
    ከአዲስ አበባ ትምህርት ቢሮ ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ እውቅናን በማግኘት በቃላዊ ሂሳብ ስሌት፣ በሶሮባንና በሁለንተናዊ የአዕምሮ ዕድገት ላይ ልዩ ልዩ ስልጠናዎችንና የሂሳብ ስሌት ውድድሮችን ሲያካሂድ የነበረው “ማይንድ ፕላስ ማትስ” ተቋም ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ በአገር አቀፍ ደረጃ የሂሳብ ትምህርት ጥያቄና መልስ ውድድር ያካሂዳል፡፡
ውድድሩ በአራተኛ፣ በስድስተኛ፣ በስምንተኛ፣ በ10ኛና በ12ኛ ክፍል ተማሪዎች መካከል የሚካሄድ ሲሆን ከአማራ የባህር ዳር፣ ከኦሮሚያ የአሰላና አዳማ፣ ከትግራይ የመቐለ፣ እንዲሁም የአዲስ አበባና የድሬደዋ ከተማ ተማሪዎች እንደሚሳተፉና በመጀመሪያው ዙር 10ሺህ ያህል ተማሪዎች ለውድድር ቀርበው እንደነበር “ማይንድ ፕላስ ማትስ” ገልጿል፡፡ እስካሁንም ከአዲስ አበባ 3126፣ ከመቀሌ 1569፣ ከባህር ዳር 659፣ ከአሰላ 300፣ ከአዳማ 300 ከድሬደዋ 450 በድምሩ 6404 ተማሪዎች ክልላቸውን ወክለው የሚቀርቡ ሲሆን በየክፍል ደረጃቸው 15 ተማሪዎች ለመጨረሻው ዙር ቀርበው፣ የአሸናፊዎች አሸናፊ የመለየት ስራ እንደሚሰራም ተቋሙ ገልጿል፡፡
የፈተናዎቹ ጥያቄዎች በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና በኮተቤ ሜትሮ ፖሊታንት ዩኒቨርሰቲ መምህራን በጥንቃቄ የተዘጋጁ መሆናቸውንም ተቋሙ ጨምሮ ገልጿል፡፡ በውድድሩ 1ኛ ለሚወጣ 10 ሺህ ብር፣ 2ኛ ለሚወጣ 7 ሺህ ብር፣ በ3ኛነት ለሚያሸንፍ የ5 ሺህ ብር ሽልማት መዘጋጀቱን የገለፀው “ማይንድ ፕላስ ማትስ”፤ የመጨረሻውና የሽልማቱ ሥነ ስርዓት በእለተ ፋሲካ በተመረጠ የቴሌቪዥን ጣቢያ በቀጥታ እንደሚተላለፍ አስታውቆ፣ ውድድሩ መካሄዱም ሆነ በቴሌቪዥን ቀጥታ መተላለፉ ሌሎች ተከታይ ተማሪዎችን በማነቃቃት፣ በሂሳብ ትምህርት ላይ ፍላጎት እንዲያድርባቸውና ለውድድር ዝግጁ እንዲሆኑ ያደርጋልም ተብሏል፡፡

በአንዱአለም አባተ (የአፀደ ልጅ) የተሰናዱት “ንጉስ ዘርዓ ያዕቆብና ሌሎች ግለ - ወጎች” እና “የህሊና መንገድና ሌሎች ልቦለዶች” የተሰኙ መፅሀፎች ሰኞ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል እንደሚመረቁ የምርቃቱ አዘጋጅ መገዘዝ መልቲ ሚዲያና ቴአትር ፕሮሞሽን አስታወቀ፡፡ በዕለቱ የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ “ንጉስ ዘርዓ ያዕቆብና ሌሎች በተሰኘው መፅሀፍ ላይ ልዩ ዳሰሳ የሚያቀርቡ ሲሆን ፕሮፌሰር ሙሉጌታ ጀዋሬ ደግሞ መፅሀፉ ለቴአትር ትምህርትና ለደራሲያን ያለውን ፋይዳ ለታዳሚው ያካፍላሉ ተብሏል፡፡ በአ.አ.ዩ የጋዜጠንነትና ተግባቦት መምህር የሆኑት ዶ/ር ተሻገር ሽፈራው ደግሞ “የህሊና መንገድ እና ሌሎችም” በተሰነው መፅሀፍ ላይ ዳሰሳ እንደሚያቀርቡም ታውቋል፡፡ “ንጉስ ዘርዓ ያዕቆብ” የተሰኘው መፅሐፍ ደራሲው በመረጣቸው ተሪካዊያን ግለሰቦች ላይ በመመርኮዝና በተውኔታዊ አቀራረብ ያሰናዳቸው ታሪኮች የተካተቱበት ሲሆን ቁልፍ ርዕሰ ጉዳዮችም በፍትህ፣ በእውነት፣ በበቀል፣ በክህደትና በቃል ኪዳን ላይ ያተኮሩ ናቸው፡፡ ታሪኮቹ ምናባዊ ልብ ወለድ ቢሆኑም ከታሪክና ከቅዱሳት ድርሳናት ዋናውን የትረካ ጭብጥ ይዘው በመነሳታቸው በስነ - ፅሁፍ ዓለም “ንቡር ጠቃሽ” ከሚባለው የስነ ፅሁፍ ዘውግ ይመደባልም ተብሏል፡፡ በ124 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፉ፤ በ60 ብርና በ15 ዶላር እየተሸጠ ነው፡፡ ደራሲው “የህሊና መንገድ እና ሌሎም አጫጭር ልቦለዶች” የተሰኘ አዲስ መፅሐፍም ለንባብ አብቅቷል፡፡ በዚህ መፅሀፍ ውስጥ በተለያየ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ 13 ያህል አጫጭር ልቦለዶች ተካተውበታል፡፡ በ118 ገፆች የተመጠነው መፅሐፉ በ50 ብርና በ10 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡

ሁለት አንበሶች እኔ እገዛ፣ እኔ እገዛ ተጣሉ! አሉ፡፡ አንዱ፤ ዕድሜዬ ረዥም ነውና ለመግዛት የኔ ነው የሚፈቅደው ባይ ነው፡፡
ሌላው፤ “ባያት በቅድመ - አያቴ ስለተመረቅሁ - ገዥው እኔ ነኝ” አለ፡፡
“እንግዲያው ይለይልን” ሆነ፤ የመጨረሺያው መፍትሄ፡፡ ይሄ ሁሉ ሲሆን ጥንቸል ባቅራቢያው ሆና ትታዘባለች፡፡
ክፉ ትግል ገጠሙ፡፡ ብዙ ፍልሚያ ካካሄዱ በኋላ ሁለቱም ደክመው መሬት ላይ ተዘረሩ፡፡ Ending infatigue እንደሚባለው ነው፡፡ ጥንቸል ውጤቱን ስትጠባበቅ ቆይታ ሁለቱም አቅም አጥተው መውደቃቸውን አየች፡፡ ይሄኔ በኩራትና በእብሪት፣ በዙሪያቸው ተቀምጣ ሰው፣ ባለፈ ባገደመ ቁጥር፤
“ትልቅና ጉልበተኛ መሆን ሳይሆን ብልሃተኛ መሆን ነው የድል ሚስጥሩ” እያለች ማስረዳቷን ቀጠለች፡፡
ከጥቂት ጊዜ በኋላ ግን አንደኛው አንበሳ ከተኛበት ነቃ፡፡ ይሄኔ ጥንቸል፤
“እርስዎ እንደሚነሱ አውቄ አካባቢውን ስጠብቅ እስካሁን ቆይቻለሁ፡፡ እንግዲህ በሰላም ከነቁ ብሄድ ይሻላል፡፡” አለች፡፡
አንበሳም፤ ቀጨም አድርጎ ያዛትና፤ “ለሰዎች ሁሉ፤ ብልሃት የሌላቸው አንበሶች ይወድቃሉ ስትይ የሰማሁ መሰለኝ፡፡ ለዚያም ዋጋ ትከፍይበታለሽ፡፡ በኛ ደክሞ መውደቅ አንቺ ዝና ልትገዢ መጣርሽ ምን እንደሚያስከፍል ማወቅ አለብሽ!” አላት
ጥንቸልም፤
“በእንቅልፍ ልብዎ መሆን አለበት የሚያወሩኝ” አለች፡፡
አንበሳም፤
“አይ ጥንቸል! በእንቅልፍ ልቤም’ኮ ልቤ የራሴ ነው!” ብሎ አድቅቆ ደቁሶ በላት!
*        *      *
ጊዜ አመቸኝ ብሎ መፎከር ውጤቱ አደገኛ ነው፡፡ ጊዜ ሰጠኝ ብሎ ዝና ለማፍራት መሞከር በመጨረሻ ዋጋ ያስከፍላል፡፡ ዝና መቼ መጠቂያ እንደሚሆን ስለማይታወቅ ብርቱ ጥንቃቄ ይጠይቃል፡፡ አንዲት ያልታወቀች ገጣሚ፤
“ዝናኮ እንደንብ ነው
ዜማ አለው
እሾክ አለው
እግዚኦ ለሰማያቱ ያለህ፣
ለካ ክንፍም አለው!” ብላለች፡፡
የዝና ክንፍ የት እንደሚያደርሰን አይታወቅም፡፡ ለጊዜው የሚያደንቀን ህዝብም መቼ ጀርባውን እንደሚያዞርብን አይታወቅም፡፡ ዝና ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ለዚህ ነው! ዛሬ የገነንን ይመስለናል፡፡ ነገ ግን ስንወድቅ ምሳሩን እኛው ላይ እንደሚሰነዝር አንርሳ፡፡ ቂሙን የማይረሳ ህዝብ፣ መቼም ይሁን መቼ፣ ለሰራነው ዋጋ ሳያስከፍለን አይቀርም፡፡ ለጊዜው ቢያቀረቅርም ቀኑ ሲመሽብን፣ ታሪክን ጠቅሶ ቁጭቱን ይወጣል፡፡ ሁሉም የጊዜ ጉዳይ ነው፤ ይለናል፡፡ ስለዚህ ዛሬውኑ መናዘዝ፣ ዛሬውኑ ህዝብን ይቅር በለኝ ማለት የመዳኛችን አንዱ መንገድ ነው! ውጊያውን እንጂ ጦርነቱን እንዳላሸነፍን እንወቅ! (Won the battle but not the war) ጦርነቱ ያለው ህዝብ ልቦና ውስጥ ነውና! “የጀርመን ግንብ ቢፈርስም፤ ህዝቡ ጭንቅላት ውስጥ አልፈረሰም” የሚባለው ለዚህ ነው! አሁንም ደግመን ደጋግመን፣ ለህዝቡ ምን ደግ ነገር ሰርተናል? ብለን እንጠይቅ፡፡ የወደፊት ዕድሜያችን የሚለካው በዚያ ነው፡፡
የነገ ህይወታችንን የሚወስኑት ዛሬ የምናያቸው ምልክቶች ናቸው፡፡ የሰው ምሬት የት ደርሷል? ኢኮኖሚያችን የህዝብን በልቶ ማደር ያገናዘበነውን? ተጠይቀው ያልተመለሱት የፖለቲካ ጥያቄዎች፣ ዛሬም እንደተንጠለጠሉ ናቸው? ወይስ ተመልሰውልናል? ዲሞክራሲው እየተዳከመ ነው እየጠነከረ የመጣው? ፍትሐችን ሚዛኑን በመጠበቅ ረገድ ወገናዊ ነው አይደለም? “እናቱ የሞተችበትም ገበያ የሄደችበትም እኩል ያለቅሳሉ”፤ የሚባልበት አገር አሁንም አለን? ወይስ ሁኔታው ተለውጧል? እስረኞችን መፍታት አንድ ይበል የሚሰኝ እርምጃ ነው፡፡ በቀጣይ የተሻለ ሁኔታ እንጠብቃለን፡፡ ሌሎች የማይታሰሩበትን ሁኔታ መፍጠር ወሳኝ ሂደት ነው፡፡ ያማረ ሁኔታ ይፈጠር ዘንድ ሁላችንም መረባረብ ይኖርብናል፡፡ ያም ሆኖ መጪውን ችግር የሚጠቁሙ ሂደቶችን እናስተውል፡፡ Coming events cast their shadows ይላሉ ፀሐፍት፡፡ መጪው ጊዜ ዛሬ ላይ ጥላውን ይጥላል፤ እንደማለት ነው፡፡ ነገን ዛሬ እንጠንቀቅ፡፡ አለበለዚያ “በመስከረም የሚቆስል በሰኔ ያሳክከዋል” የተባለው ተረት ዕውን ይሆናል፡፡ እናስብ! እናስብ! ደጋግመን እናስብ!

 • የገዢዎች አፈና ሲቆም የህዝቦች ግንኙነት ይጠናከራል
      • አጀንዳችን የኢትዮጵያን አንድነት ማምጣት ነው
      • በአጠቃላይ የዘር ፖለቲካው አላንቀሳቅስ ብሎናል

     ሰሞኑን አረና ትግራይ ለፍትህና ለሉአላዊነት፣ የማዕከላዊ ኮሚቴ ስብሰባውን አድርጎ፣ የሀገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ የገመገመበትን መግለጫ አውጥቷል፡፡ ለመሆኑ መግለጫው ስለ ሀገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ ምን ይላል? በትግራይ ክልላዊ መንግስት የተደረገውን የአመራር ለውጥስ እንዴት ያየዋል? በእነዚህና ሌሎች ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፣ ከፓርቲው ሊቀ መንበር አቶ አብርሃ
ደስታ ጋር ተከታዩን አጭር ቃለ ምልልስ አድርጓል፡፡ እነሆ፡-


    ፓርቲያችሁ የሀገሪቱን ወቅታዊ ሁኔታ እንዴት ነው የገመገመው?
አንደኛ፣ በሀገሪቱ የፖለቲካ ቀውስ የመኖሩን ጉዳይ ነው የገመገምነው፡፡ የፖለቲካ ቀውሱ ደግሞ በኢህአዴግ አፈና ምክንያት የተፈጠረ ነው፡፡ አሁን የህዝብ አልገዛም ባይነት አለ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የኢህአዴግ ህዝብን መምራትና ማስተዳደር አለመቻል እየታየ ነው፡፡ ይሄ ነገር በአግባቡ ካልተመራ ወደባሰ ፖለቲካዊ ቀውስ ሊመራን ስለሚችል፣ ምን ማድረግ አለብን በሚለው ጉዳይ ላይ ተወያይተናል፡፡ ሀገሪቱን ለማዳን፣ ቀውሱን ለመፍታት ምን መደረግ አለበት በሚለው ላይ ሰፊ ውይይት አድርገናል፡፡
ታዲያ በውይይታችሁ ምን ላይ ደረሳችሁ…?
እንግዲህ ኢህአዴግ ለሀገሪቱ ችግር መፍትሄ ከማምጣት ይልቅ አባባሽ ሁኔታዎችን እየፈጠረ በመሆኑ፣ እኛ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆን፣ የሀገር አንድነት ማምጣት እንደሚገባንና የእርስ በእርስ ግጭት እንዲቆም ሁሉም ህዝብ እንደ አንድ ህዝብ በጋራ እንዲታገል መጣር  አለብን ብለናል። በሌላ በኩል በኢትዮጵያ አንድነት ከሚያምኑ፣ የኢትዮጵያ መፃኢ እድል ከሚያሳስባቸው የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር ትብብር በመፍጠር፣ አንድ ላይ መስራት እንዳለብን ተስማምተናል፡፡ በትግራይ አካባቢ ህዝብን ፖለቲካ ማስተማርና ማደረጃት እንደሚገባን፣ ከምንም በላይ የኢትዮጵያን አንድነት ማስጠበቅ እንዳለብን አቅጣጫ አስቀምጠናል፡፡
ከሰሞኑ ተፈፅመዋል የተባሉ ብሄር ተኮር ጥቃቶችን  እንዴት ተመለከታችሁት? መፍትሄውስ ምንድን ነው?
እርግጥ ነው የትግራይ ተወላጆች ጥቃት ደርሶባቸዋል፤ ግን ይሄ የሆነው በህውሓት ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ መፍትሄው፣ ከህዝቡ ጋር ሆኖ ህውሓትን መታገል ነው ብለን ገምግመናል። ሁሉም የሚስተካከለው የተቀናጀ ትግል ሲደረግ ብቻ ነው።
በቅርቡ በትግራይ ክልል የተደረገው የአመራር ለውጥ ምን ውጤት ያመጣል ትላላችሁ?
የህዝብ ጥያቄ በአመራር ለውጥ ብቻ አይመለስም፡፡ ህውሓት ህውሓት ነው፤ ሰዎቹም የህውሓት አባሎች ናቸው፡፡ ስለዚህ እኛ ከዚህ የአመራር ለውጥ፣ ብዙም ውጤት አንጠብቅም፡፡ ህዝቡ የፈለገውን እንዲመርጥ መፍቀድ አለባቸው  ብለን እናምናለን፡፡ አሁን በኦሮሚያ እየተደረገ  ያለው ጥሩ ነገር ነው፡፡ በህውሓትም እነሱ መርተው ለውጥ ማምጣት እንደማይችሉ አውቀው፣ የለውጥ ኃይል እንዲመጣ መንገዱን መክፈት ነው ያለባቸው። እንደ ቀድሞ ጨቁኖ መግዛት የማይቻልበት ደረጃ ላይ እየተደረሰ በመሆኑ ወይ ተገደው ይለወጣሉ ወይ እነሱ ራሳቸው በለውጡ ይሄዳሉ፡፡
ከሰሞኑ “ትግራይን መገንጠል” የሚል ነገር በአንዳንድ ወገኖች፣ በማህበራዊ ሚዲያ ተነስቷል። ይሄን ጉዳይ ፓርቲያችሁ እንዴት ይመለከተዋል?
አረና በኢትዮጵያ አንድነት የሚያምን ፓርቲ ነው፤ ትግራይ የኢትዮጵያ መሰረት ነው ብለን ነው የምናስበው፡፡ ትግራይ ከሚለው ስም በፊት ኢትዮጵያ ብሎ ነው የትግራይ ህዝብ የሚያምነው፡፡ ይሄ ሃሳብ  በተለያዩ አካባቢዎች ከሚደርሱ ብሔር ተኮር  ጥቃቶች የተነሳ የመጣ ነው፡፡ ተገፋሁ የሚል አካል ይሄን ማንሳቱ የሚገርም ባይሆንም ጊዜያዊ ስሜት መሆኑ ግን አያጠያይቅም፡፡ የትግራይ ህዝብ በኢትዮጵያዊ አንድነቱ ፅኑ መሰረት አለው። ወደ መገንጠል ወይም ሌላ አማራጭ የሚሄድ አይደለም። ይሄ ሃሳብ የመከፋት ስሜት መኖሩን የሚጠቁም እንጂ የትግራይ ህዝብን አቋም የሚገልፅ አይደለም፡፡ የኛም እምነት የኢትዮጵያ አንድነት ነው። አጀንዳችንም የኢትዮጵያን አንድነት ማምጣት ነው፡፡
ከዚህ ቀደም አንድ ጠንካራ ሃገራዊ ፓርቲ የመፍጠር ዓላማ  እንዳላችሁ ጠቁማችሁ ነበር፡፡ ይህ ሃሳብ ከምን ላይ ደረሰ?
እርግጥ ነው እቅድ አውጥተን ነበር፡፡ ነገር ግን አልተሳካም፡፡ ከፓርቲዎች ጋር ለመቀራረብ ያደረግነው ጥረት ውጤት አላመጣም፡፡ አጋጣሚ ሆኖ ፖለቲካው ወደ ብሄር ፖለቲካ ገባ፡፡ ሁሉም በብሄር ማሰብ ጀመረ፡፡ በዚህ የተነሳ ዕቅዱን መተግበር አስቸጋሪ ሆነብን፡፡ ኢትዮጵያዊነት የሚለው ነገር ብዙ ትኩረት ባለማግኘቱ፣ ውጤታማ መሆን አልቻልንም፡፡ ነገር ግን አሁንም እንቅስቃሴው አልቆመም፤ ሆኖም  ይሄን እኛ ብቻ ልናደርገው አንችልም፡፡ ሌሎች ፓርቲዎችም ይሄን ሃሳብ ይዘው መንቀሳቀስ እስኪጀምሩ ድረስ ክልላዊ ፓርቲ ሆነን እንቀጥላለን፡፡
አሁን አረና እያደረገ ያለው ፖለቲካዊ  እንቅስቃሴ ምን ይመስላል?
አሁን ጠንካራ እንቅስቃሴ እያደረግን አይደለም። ያላደረግንባቸው ምክንያቶች ደግሞ በርካታ ናቸው። አንዱ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ነበር፡፡ በሌላ በኩል፣ ህውሓት በኛ ላይ የሚነዛው ፕሮፓጋንዳ አላንቀሳቅስ ብሎናል፡፡ በኢትዮጵያዊነት ጉዳይ ላይ ስንንቀሳቀስ፣ ህውሓት፣ “እነዚህ ስለ ትግራይ ህዝብ ጥቃት አያስቡም” ይለናል፡፡ ለትግራይ ህዝብ መቆርቆር ስናሳይ ደግሞ በአንዳንድ ወገኖች “ፀረ ኢትዮጵያ” እንባላለን፡፡ ይሄ ለፖለቲካዊ እንቅስቃሴያችን ከፍተኛ  እንቅፋት ሆኖብናል፡፡ በአጠቃላይ የዘር ፖለቲካው አላንቀሳቅስ ብሎናል፡፡
በሌላ በኩል ግን የትግራይ ህዝብ፣ የፖለቲካ ለውጥ በመፈለግ ሰፊ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው፡፡ አሁን ደጋፊና ለውጥ ፈላጊ ህዝብ ስላለ፣ አረና በጥሩ ሁኔታ ላይ ይገኛል ማለት ይቻላል፡፡ አሁን የብሄር ፖለቲካው የበላይነት ስለያዘ፣ ለጊዜው ህዝብን ስለ ኢትዮጵያ አንድነት እየሰበክን ነው መንቀሳቀስ የምንፈልገው፡፡ አጀንዳው ከባድ ቢሆንብንም በኢትዮጵያ አንድነት ተስፋ አለን፡፡ በህዝቦች መካከል እየተፈጠረ ያለው ችግርም የገዥዎች የአፈና ውጤት ነው ብለን እናምናለን፡፡ ይሄ አፈና ሲቆም የህዝቦች ግንኙነት ይጠናከራል የሚል እምነት አለን፡፡

  ከእንግሊዝ አምባሳደር ጋር በእስረኞችና በሀገሪቱ የፖለቲካ ጉዳይ ላይ ተወያይተዋል

    በቅርቡ ከእስር የተለቀቁት ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ወደ መደበኛ የፓርቲ ሥራቸው ለመመለስ መወሰናቸውን የገለጹ ሲሆን በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ከሆኑት ሱዛን ሞርሄድ ጋር መወያየታቸውም ታውቋል፡፡
በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ ባወጣው መረጃ፤ አምባሳደሯ በወቅቱ የሀገሪቱ ጉዳይ ላይ ከዶ/ር መረራ ጉዲና ጋር መወያየታቸውን ጠቁሟል። ውይይቱን በተመለከተ ለአዲስ አድማስ ያብራሩት ዶ/ር መረራ፤ ስለ ማረሚያ ቤቶች የእስረኞች አያያዝ፣ ስለ ወቅቱ የሀገሪቱ ሁኔታና ወደፊት ሊሆን ስለሚገባው ጉዳይ ከአምባሳደሯ ጋር በስፋት መነጋገራቸውን ገልጸዋል፡፡ በተለይ ህብረተሰቡ በመንግስት ላይ ያለውን ተቃውሞ የሰው ህይወት መቅጠፍን የሚያስከትል ግጭት ሳይፈጠር፣ በሰላማዊ መንገድ በሚያሰማበት ሁኔታ ላይ በትኩረት ተወያይተናል ብለዋል - ዶ/ር መረራ።
በተመሳሳይ ከሁለት ሳምንት በፊት በኢትዮጵያ የጀርመን አምባሳደር ከሆኑት አምባሳደር ቫግ ነር ጋር መወያየታቸውን  መዘገባችን  ይታወሳል፡፡
ከእስር በተለቀቁ ወቅት በፖለቲካ ትግላቸው ይቀጥሉ እንደሆነ አለመወሰናቸውን የተናገሩት ዶ/ር መረራ፤ በአሁኑ ወቅት በኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) የሊቀ መንበርነት ሥራቸው ለመቀጠል መወሰናቸውን ለአዲስ አድማስ አስታውቀዋል፡፡
በሌላ በኩል፣ ዶ/ር መረራ ጉዲና፣ ከአደአ በርጋ ህዝብ በቀረበላቸው ጥሪ መሰረት፣ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ወደ አካባቢው በተጓዙበት ወቅት በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ የአካባቢው ነዋሪዎች ከፍተኛ የአድናቆት አቀባበል እንዳደረጉላቸው የኦፌኮ ም/ሊቀመንበር አቶ ሙላቱ ገመቹ ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡   
በተመሳሳይ ዶ/ር መረራ፣ ከሁለት ሳምንት በፊት በአምቦ ከተማ፣ተቀራራቢ ቁጥር ያለው ህዝብ ደማቅ   አቀባበል እንዳደረገላቸው ይታወቃል፡፡