Administrator

Administrator

  የምድር አውሬ ሁሉ መሰብሰቢያና መናገጃ አንድ ገበያ ነበር ይባላል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አውሬ ሁሉ እገበያ ሲውል አያ ጅቦ ግን ሳይሄድ ቀረ፡፡ የማታ ማታ ገበያተኛ ሲመለስ ከጎሬው ወጣና ከመንገድ ዳር ተቀመጠ፡፡ ገበያ ምላሽ ሲሆን እንኮዬ ዝንጆሮ ስትመጣ፣ የገበያውን አዋዋል ጠየቃት፡፡ እንደምትቸኩል ነግራው፣ ጦጢትን ጠይቃት አለችው፡፡ ጦጢትን ጠየቃት፡፡ እሷም፤ እንኮዬ ሚዳቋን ጠይቅ ብላው ሄደች፡፡ ሚዳቆን ጠየቃት፡፡ እቸኩላለሁ፤ እንኮዬ አህዪትን ጠይቃት አለችው፡፡
በመጨረሻው አህዪት መጣች፡፡ ገበያው እንዴት ዋለ? አላት፡፡ “ቆይ ቁጭ ብዬ ላጫውትህ!” ብላ ተቀመጠች፡፡ ሁሉን ካወራችለት በኋላ፤ “እንደኔ ይሄን ገደል እመር ብለሽ ማለፍ ትችያለሽ?” አለና ጠየቃት፡፡
“አሳምሬ!” አለችው፡፡
አጅሬ የሞት ሞቱን እንጣጥ ብሎ ዘለለው፡፡ አህዪት ግን እዘላለሁ ብላ ወርዳ ተከሰከሰች፡፡ አያ ጅቦ ሆዬ፤ ታች ወርዶ ሆዷን ዘንጥፎ ይበላ ጀመር፡፡ ይሄኔ ውሻ ከአፋፍ ብቅ አለች፡፡ ስታስተውል አበላሉ አስጎመዠትና፣ ምራቋ ጠብ ጠብ ሲል አናቱ ላይ አረፈ፡፡፡ ቀና ብሎ ቢያይ፤ ውሺት አለች፡፡
“በይ ነይ ውረጂና እየመተርሺ አብይኝ” አላት፡፡
“እሺ ጌታዬ” ብላ ወርዳ እየመተረች ስታበላው ቆይታ፤ አያ ጅቦ ዞር ሲልላት የአህዪትን ልብ ዋጥ ስልቅጥ አደረገችው፡፡ ጅቦ መለስ ብሎ ቢያይ ልቧን አጣው፡፡
ውሾን፤
“ልቧ ወዴት ሔደ?” ብሎ ጠየቃት፡፡
“ልብ ባይኖራት ነው እንጂ ልብማ ካላት አንተ ዘንድ መጥታ መቼ ትቀመጥ ነበር?” አለችው፡፡
አያ ጅቦ ግን፤ “ቅድም አይቼው ነበር፡፡ ታመጪ እንደሆን አምጪ፡፡ አለበለዚያ፤ አንቺንም እበላሻለሁ” አላት፡፡
“ምነው አያ ጅቦ፤ እኔን በቅቤና በድልህ አጣፍጠህ ነው እንጂ፣ እንደ አህዪት ደረቁን ትበላኛለህ?” አለችው። ሆዳሜ ዕውነት መሰለውና፤
“ቅቤውና ድልሁ ከየት ይመጣል?” አለና ጠየቃት፡፡
“ከእመቤቴና ከጌታዬ ቤት እኔ ሄጄ አመጣዋለኁ” አለችው፡፡
“ሄደሽ የጠፋሽ እንደሆነ ማ ብዬ እጠራሻለሁ?”
“እንኮዬ ልብ-አጥቼ፤ ብለህ ትጠራኛለህ!”
“በይ እንግዲያውስ ሄደሽ አምጪ” አላት፡፡
“እሺ ታዛዥ ነኝ!” ብላ ሄደች፡፡
ሄደችና ቅርት አለችበት፡፡
“ኧረ እንኮዬ ልብ-አጥቼ” እያለ ተጣራ፡፡
“ከእመቤቴና ከጌታዬ ቤት ለምን ወጥቼ!” ብላ፤ የስድብ ወርጂብኝ አወረደችበት፡፡
ከጊዜ በኋላ ግን ውሺት ስትልከሰከስ፤ አያ ጅቦ ያዛት፡፡ ዐይኗ ፈጠጠ፡፡
አያ ጅቦም “ዐይንሽ በምን እንዲህ አማረ?” አላት፡፡
“ጌታዬ፤ በአሥር የአጋም እሾህ ተነቅሼ ነዋ!” አለችው፡፡
“እባክሽ እኔንም ንቀሺኝ?”
ውሺት፤ አጋም እሾህ ሰብራ አመጣችና ዐይኖቹን ትጠቀጥቃቸው ጀመር፡፡
“ኧረ አመመኝ ውሺት”
“ሲያጌጡ ይመላለጡ ነው! ማማር እንዲያው ይገኝ መሰለህ?”
ብላ ሁለቱንም ዐይኑን አሳወረችው፡፡ ከዚያም ሠንጋ ጥለው፣ በጎድን ተዳቢት የሚደባደቡ ሰዎች ጋ ልውሰድህ ብላ ለገበሬዎች አሳልፋ ሰጥታ አስገደለችው!
*    *    *
“ያሰቡትንና ያቀዱትን ቸል ሳይሉና ሳይታለሉ ከፍፃሜ ማድረስ፣ የአስተዋይ ተግባር ነው፡፡ እኩይ ያልሆነ ጓደኛ መያዝ፣ ነገርን ሳያመዛዝኑና ሳያሰላስሉ ፈጥኖ ማመንና መቀበል የሚያስከትለውንም አለማሰብ፣ ከየዋህነትና ከቂልነት አስቆጥሮ ከጥቃት ያደርሳል፡፡ አታላይ ለጊዜው በመብለጥለጥ ምኞቱን ቢያረካም የፈፀመው ደባ እንደሚደርስበት የጅቡን አወዳደቅ መመልከት ይበቃል፡፡ ከእንስሳትም ውስጥ በአስተዋይነታቸውና በብልህነታቸው የሚመሰገኑ ፍጥረታት ይገኛሉ፡፡ እነሆ ውሻይቱ፤ በዘዴ ከአደጋ ከአመለጠች በኋላ፤ ኃይለኛ የሆነ ጠላቷን አሞኝታ ከሞት አደጋ አድርሳዋለች”፡፡ (ብላቴን ጌታ ማኅተመ ሥላሴ ወ/መስቀል) አቅደን በዕንጥልጥል የተውነው ስንት ጉዳይ ነበረን? የማያዋጣ ጓደኛ ምን ያህል ጊዜ ያዝን? ምን ያህል ደባዎች ተፈፀሙብን? ከዚያስ ምን ያህል ተማርን? እነዚህን ጥያቄዎች ደጋግመን ብንጠይቅ፣ ብዙ ችግሮችን ለማስወገድ እንችላለን!
አብዛኞቹ ግለሰቦች በፓርቲ የፖለቲካ ህይወታቸው የመታለል እጣ ይገጥማቸዋል፡፡ በትልቅነታቸውና ሆይ ሆይ በሚባሉበት ሰዓት፣ ከቶም መውደቅ የሚል ነገር እንዳለ ትዝ አይላቸውም! በታሪክ የነበሩ መሪዎች፣ የፖለቲካ ኃላፊዎች፣ ታላላቅ ሰዎች እንዴት ወደቁ? የእኔስ አካሄድ ምን ይመስላል? አለማለት፤ ቢያንስ የዋህነት ነው! ከታሪክ አለመማር ነገን ለመገመት አለመቻል ነው፡፡ ነገን አለመገመት የራስን ፍፃሜ አለማጤን ነው፡፡ ስለሆነም የድንገቴ አወዳደቅ አይቀሬ ይሆናል፡፡ ማጣፊያው ያጥራል! በደጉ ሰዓት ያላቆዩዋቸው ጓደኞች፣ በክፉው ሰዓት አይኖሩምና፤ የማታ ማታ አጋዥ ደጋፊ ማግኘት አዳጋች ይሆናል፡፡ ህዝብ የደገፈን ሲመስለን ጥንቃቄ ስለማናደርግና የእኔው ነው ብለን ስለምንኮፈስ ነው! ሲመሽብን ግን በምን ያህል ፍጥነት እንደሚተፉን፣ በምን ያህል ፍጥነትስ ገፍትሮ እንደሚጥለን ሳንገነዘብ ከአደባባይ ሸንጎ እንወገዳለን። የሚገርመው ስንወድቅም ህዝብ ከድቶናል ብለን አለማመናችን ነው!! ከአንገት በላይ ፍቅር ከአንገት በላይ ይቀራል! የህዝብን መሠረተ-ነገር አለማጤን ክፉ ማጥ ውስጥ ይከታል!!
ማንኛውም ነገር ያረጃል፡፡ ያፈጃል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲ ፍቅርም እንደዚያው ነው፡፡ ትላንት የደምና የመስዋዕትነት ጓዶች የነበሩ ዛሬ በኢኮኖሚ ተፅዕኖ፣ አዳዲስ ወዳጅ በማፍራት፣ ሀቀኛ የነበረው ዓላማ ጊዜውን ጨርሶ በአዳዲስ ህሊናዊና ነባራዊ ሁኔታ ሲዋጥ፤ አሊያም የህዝብ ብሶትና ምሬት መቆሚያ መቀመጪያ ሲያሳጣው ወይም አጠቃላይ ሁኔታው ምቾት ሲነሳንና፤ ከውጪም ከውስጥም ስንወጠር፤ የዱሮው እኛነታችን ያከትማል፡፡ ከጥንት ወዳጆቻችን ጋር በሰላም ከተለያየን እሰየው ነው! በተቃራኒው ሆድና ጀርባ ሆኖ መለያየት ከመጣ ግን ወደማናውቀው ጠብ፣ መጠላለፍ እና መጠፋፋት ደረጃ እንደርሳለን! ከዚህ ይሰውረን!
ከነገራችን ሁሉ እጅግ አሳሳቢ፤ ነግ በእኔን አለማወቃችን ነው!! እኔ የተሻልኩ ስለሆንኩኝ እንደሱ አልወድቅም፣ ማለት ሁሌም እንዳታለለን አለ፡፡ ይልቁንም የወደቀውን ሰው ወንበር መሻማት፣ እሱ ባያውቅበት ነው የሥልጣንን አያያዝ፣ እያሉ፣ እዚያው ገደል ውስጥ መውደቅ የተለመደ ሆኗል! አይጣል ነው! ታማኝነትን ከአድር-ባይነት አለመለየት እርግማን ነው! ዘላቂነትን ከዘልዓለማዊነት ጋር ማምታታት የባሰ መርገምት ነው። “ጓደኛህን ሲያማ ለእኔ ብለህ ስማ!” የሚለውን ተረት አንርሳ፡፡
“ትላንትና ሞቼ፣ ቀረሁ ሳልቀበር
እኔም የፈራሁ፣ ይሄንኑ ነበር!”… የሚለውን ግጥምም ልብ እንበል፡፡ አለመቀደም መልካም ነገር ነው። ቀድሞ መመታት እንዳለ ግን አንዘንጋ! ትላንት አለቃ የነበረው ዛሬ ምንዝር ሲሆን ማላገጡንና መሳለቁን ትተን፣ ይህ ሂደት የት ያደርሰን ይሆን? ብለን እንጠይቅ፡፡ ሁኔታዎች ካልተሻሻሉ፣ ነገሩ ሁሉ እየከፋ ይሄዳል፡፡ ጥንት “ወሎ መሰደድ ልማዱ ነው” ያሉ ባለሥልጣናት፤ እራሳቸው መቀመቅ ወርደዋል፡፡ “ገበያ እንዴት ዋለ?” ቢለው፤ “አንዱ በአንዱ ሲስቅ” የሚለው ተረት ትምህርት ካልሆነን፤ ከምን ልንማር ነው?!

ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ለ2010 የዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ በሁለቱም ፆታዎች 10 እጩዎችን ሰሞኑን ይፋ ሲያደርግ በውድድር ዘመኑ በ10ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃችውና በ2016 የዓለም ኮከብ አትሌት የነበረችው  አልማዝ አያና በሴቶች ምድብ ከአስሩ እጩዎች አንዷ ሆናለች፡፡
አይኤኤኤፍ ሰሞኑን በሁለቱም ፆታዎች ይፋ ያደረገውን የእጩዎች ዝርዝር ከ6 አህጉራት በተውጣጡ የዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ኤክስፐርቶች ፓናል መምረጡን ያስታወቀ ሲሆን በውድድር ዘመኑ በለንደኑ 16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እና በዳይመንድ ሊግ ውድድድሮች ለተመዘገቡ ውጤቶች ትኩረት እንደሰጠ ለመረዳት ይቻላል፡፡
በሴቶች ምድብ ከተያዙት አስር አጩዎች አንዷ የሆነችው ኢትዮጵያዊቷ አልማዝ አያና በቅርቡ በኢቢሲ የስፖርት ሽልማት የዓመቱ ምርጥ ሴት አትሌት ተብላ እንደተሸለመች የሚታወስ ሲሆን በአይኤኤኤፍ ማህበር የ2017 የአለም ምርጥ አትሌት ምርጫ በእጩነት የቀረበችው በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ10ሺ ሜትር የወርቅ ሜዳልያ እንዲሁም በ5ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ በመጎናፀፏ፤ እንዲሁም በርቀቱ የዓመቱን ፈጣን ሰዓት 30፡16.62 በሆነ ጊዜ በማመዝገቧ ነው፡፡ ዋና ተፎካካሪዎቿ ይሆናሉ ተብለው የተጠበቁት በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በየስፖርት መደባቸው የወርቅ ሜዳልያዎች ያገኙትና የዳይመንድሊግ ሻምፒዮኖቹ ናቸው፡፡
በተለይ በውድድር ዘመኑ በ5ሺ ሜትር የዓመቱን ፈጣን ሰዓት ያስመዘገበችና በምንም ውድድር ያልተሸነፈችው፤ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳልያ እንዲሁም የዳይመንድ ሊግ አሸናፊዋ ሄለን ኦቡሪ ከአልማዝ አያና የኮከብ አትሌትነቱን ክብር ለመንጠቅ ከፍተኛ ግምት ሲሰጣት፤ የደቡብ አፍሪካዋ ካስተር ሴማንያ በ800 ሜትር በውድድር ዘመኑ ባለመሸነፍ፤ የዓለም ሻምፒዮን ሆኖ የወርቅ ሜዳልያ በመውሰድ እና የዳይመንድ ሊግ ዋንጫን በማንሳት እንዲሁም በ1500 ሜትር በዓለም ሻምፒዮና ተጨማሪ የነሐስ ሜዳልያ በመውሰድ ነው፡፡
በከፍታ ዝላይ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እና የዳይመንድ ሊግ ድርብ አሸናፊ ማሪያ ላሳኢታካኔ፤ በ100 ሜትር መሰናክል የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እና የዳይመንድ ሊግ ድርብ አሸናፊ አውስትራሊያዊቷ ሳሊ ፓርሰን፤ በዲስከስ ውርወራ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እና የዳይመንድ ሊግ ድርብ አሸናፊ የክሮሽያዋ ሳንድራ ፔርኮቪች፤ በዝርዘመት ዝላይ የዓለም ሻምፒዮን የሆነችው አሜሪካዊቷ ብሪትኔ ሪስ፤ በምርኩዝ ዝላይ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና እና የዳይመንድ ሊግ ድርብ አሸናፊ ግሪካዊቷ ኤካቴሪን ስቴካንዲ፤ በሄፕታተሎን የዓለም ሻምፒዮን የሆነችው ቤልጅማዊቷ ናፊ ሳቱ እንዲሁም በመዶሻ ውርወራ የሚስተካከላት ያጣችው ፖላንዳዊቷ አንቲታ ዋልደርሽዚያክ ሌሎቹ ተፎካካሪዎች ናቸው፡፡በሌላ በኩል በወንዶች ምድብ በ2017 የዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ ላይ ከቀረቡት አስር እጩዎች መካከል የአምና አሸናፊ ዩሲያ ቦልት አለመካተቱ ብዙዎችን አስገርሟል፡፡ ዩሴያን ቦልት የሩጫ ዘመኑን ያበቃ በዚሁ የውድድር ዘመን ሲሆን በ16ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ በ100 ሜትር የነሐስ ሜዳልያ ማግኘቱ ብቻ እንደ ትልቅ ውጤት ቢጠቀስ ነው፡፡በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና በ10ሺ ሜትር የወርቅ ሜዳልያ፤ በ5ሺ ሜትር የብር ሜዳልያ ያገኘውና የዳይመንድ ሊግ ያሸነፈው እንግሊዛዊው ሞፋራህ የማሸነፍ እድል ሊኖረው ይችላል፡፡ በከፍታ ዝላይ ሙታዝ ኢሳ ከኳታር፤ በመዶሻ ውርወራ ፓል ፋጄክ ከፖላንድ፤ በምርኩዝ ዝላይ ሳም ኬንድሪክስ ከአሜሪካ፤ በ1500 ሜትር ኤልያህ ማንጎኒ ከኬንያ፤ በርዘመት ዝላይ ሉቮ ማናዮናጋ ከደቡብ አፍሪካ፤ በ110 መሰናክል ኦማር ኤምሲሎይድ ከጃማይካ፤ በስሉስ ዝላይ ክሪስትያን ቴይለር አከሜሪካ፤ በ400 ሜትር ዋይደን ቫን ኒኪሪክ ከደቡብ አፍሪካ እንዲሁም በጦር ውርወራ ጆሃነስ ቬተር ከጀርመን ሌሎቹ እጩ ተፎካካሪዎች ናቸው፡፡
ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር በድረገፁ እንዳመለከተው ከ6 ሳምንታት በኋላ በ2017 ኮከብ አትሌትነት የሚመረጡ አሸናፊዎችን ለመሸለም በመጀመርያ በሚቀጥሉት 9 ቀናት አስሩን እጩዎች ወደ 3 እጩዎች ለመለየት በሶስት የዓለም አትሌቲክስ ባለድረሻ አካላት ድምጽ ይሰበሰባል። የዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ማህበር ምክር ቤት 50 በመቶ እንዲሁም የአይኤኤኤፍ ቤተሰቦች የሚባሉት አባል ፌዴሬሽኖችና የተለያዩ ኮሚቴዎች አባላት 25 በመቶ የድምፅ ምርሻ በመያ የሚሰጡትን ድምፅ በኢሜል የሚያቀርቡ ሲሆን የዓለም አትሌቲክስ አድናቂዎች እና የአትሌቶች ደጋፊዎች ደግሞ በቀሪው 25 በመቶ የድምፅ ድርሻ በአይኤኤኤፍ ድረገፅ www.iaaf.org እንዲሁም ለእያንዳንዱ አስር እጩዎች በአይኤኤኤፍ ዎርልድ አትሌቲክስ ክለብ www.facebook.com/WorldAthleticsClub/ በተከፈቱ የኢንተርኔት ማህበረሰብ ገፆች ላይ በመስጠት ይሳተፉበታል።  በሶሻል ሚዲያዎቹ ላይ በፌስቡክ የየእጩዎቹን ልዩ ገፅ ላይክ በማድረግ በትዊተር ገፅ መልሶ ሪቲዊት በማድረግ ድምፅ ይሰጣል ማለት ነው፡፡
ባለፈው ዓመት በተካሄደው 29ኛው የአይ.ኤ.ኤ.ኤፍ የዓለም ኮከብ አትሌት ሽልማት ኢትዮጵያዊቷ አትሌት አልማዝ አያና በሴቶች ምድብ ማሸነፏ የሚታወስ ሲሆን  በሽልማቱ ታሪክ 6ኛውን ክብር ለኢትዮጵያ  ያስገኘችበት ነበር። በ1998 እኤአ ኃይሌ ገብረስላሴ፤ በ2004እና በ2005 እኤአ ለሁለት ተከታታይ ጊዚያት ቀነኒሳ በቀለ፤ በ2007 እኤአ መሰረት ደፋር እንዲሁም በ2015 እኤአ ገንዘቤ ዲባባ የዓለም ኮከብ አትሌት የተባሉ የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸው፡፡ አልማዝ አያና በ30ኛው የዓለም ኮከብ አትሌት ሽልማት በድጋሚ ከተመረጠች በሽልማቱ ታሪክ ሁለት ጊዜ ያሸነፈች  ብቸኛዋ ሴት እንዲሁም 7ኛዋ ኢትዮጵያዊ አትሌት ትሆናለች፡፡
በ2016 የአይኤኤኤፍ የዓለም ኮከብ አትሌት ምርጫ ላይ በሴቶች ምድብ አልማዝ አያና ያሸነፈችው በ31ኛው ኦሎምፒያድ በ10ሺ ሜትር የወርቅ ሜዳልያ ስትጎናፀፍ የዓለም እና የኦሎምፒክ ሪከርድ በማስመዝገቧ፤  በተጨማሪ በ5ሺ ሜትር የነሐስ ሜዳልያ በማግኘቷ እንዲሁም  በ2016 የአይኤኤኤፍ ዳይመንድ ሊግ ደግሞ በ3ሺ እና 5ሺ ሜትር 4 ውድድሮች አድርጋ በሰበሰበችው 50 ነጥብ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫ እና የ43ሺ ዶላር ተሸላሚ ለመሆንም በመብቃቷ ነበር፡፡

በኢትዮጵያ የግልም ሆነ የመንግስት… አንድም ሆስፒታል ደረጃውን መቶ በመቶ ባሙዋላ መልኩ የተደራጀ አይደለም፡፡
ባለፉት ሁለት ሳምንታት በወጣው እትም የህክምና ባለሙያዎች የህግ ተጠያቂነት በአለም አቀፍ ደረጃ ምን መልክ አለው? በአገራችንስ? የሚሉትን ነጥቦች ለንባብ ብለናል፡፡ በዚህ ዙሪያ የሚነሱ የመጨረሻ ሀሳቦችን ከህግ ከባለሙያው አቶ አበበ አሳመረ ማብራሪያ እናገኛለን። በኢትዮጵያ በሕክምና አገልግሎት አሰጣጥ በኩል የሚደርሱ ችግሮች ይህን ይመስላሉ የሚል ጥናት ባይኖርም የደረሱ ችግሮች ግን የሉም ማለት አይደለም።  ባለፉት ሁለት ሳምንታት የወጣውን እትም ያነበቡ የአንድ ቤተሰብ አባል በልጃቸው ላይ የደረሰውን ገጠመኝ በጽሁፍ ልከውልናል፡፡ እንደሚከተለው ነው፡፡  
‹…ሁኔታው ያጋጠመው በቅርብ ነው፡፡ ነሐሴ 2009/ ዓ/ም፡፡ ሕጻኑ በእድሜው 10/አመት ነው፡፡ ክስተቱ ሲያጋጥም ለእረፍት ከአያቱ ቤት ሰሚት ከሚባለው ስፍራ ነበረ፡፡ ከአባቱ እናት ጋር ሆኖ የፍልሰታን ጾም እየጾም ቁርባን ይቆርባል፡፡ አንድ ቀን ግን ያልታሰበ ሁኔታ ያጋጥ ማል፡፡ በድንገት ልጁ ታመምኩ አለ፡፡ ትኩሳት መድከም የመሳሰሉት ነገሮች ይታዩበታል፡፡ ቀረብ ወደሚለው ሐኪም ቤት ይወስዱታል፡፡ ከሐኪም ቤቱም የተገኘው መልስ የጨጉዋራ ሕመም መሆኑንና የሚመገበውን እና የማይመገበውን ምግብ ነግረው የጨጉዋራ መድሀኒት ይሰጡታል፡፡ ይህ ሕጻን እውን የጨጉዋራ በሽታ ያዘው? እንዴት? እየተባለ በቤተሰብ ውስጥ ሀሳቡ እየተንገዋለለ እሱም ህመሙ ምንም ሳይሻለው እንዲያውም እየባሰበት ሁለት ቀን አደረ፡፡ በሶስተኛው ቀን ግን ልጁ ምንም አይንቀሳቀስም፡፡ ዛለ፡፡ አይናገርም፡፡ ትኩሳቱ እጅግ ከፍ ብሎአል፡፡ እንደገና ወደሌላ ሐኪም ቤት ተወሰደ፡፡ የተገኘው መልስ እጅግ አስደንጋጭ ነበር። ትርፍ አንጀቱ በጊዜው ሕክምና ስላላገኘ ፈንድቶአል (rupture) አድርጎአል የሚባል ነበር፡፡ ቤተሰብ በሙሉ ተደናገጠ። ሐኪሞቹም እጅግ አዘኑ፡፡ ነገር ግን መሞቱ ካልቀረ ይከፈትና ይሞከር ተብሎ ከሁለት ሰአት በላይ የፈጀ ኦፕራሲዮን ተደርጎ አሁን ደህና ነው፡፡ ከመሞትም ተርፎአል፡፡ ለዚህ ጉዳይ ተጠያቂው ማነው? በሚል ሀሳቡን ለተለያዩ ሐኪሞች  አንስተን ነበር፡፡ የሐኪሞቹ መልስ ግን አስገራሚ ነበር፡፡
ግማሾቹ …በእርግጥ የጨጉዋራና የትርፍ አንጀት ሕመም ስሜት ይመሳሰላል፡፡ ለዚህም ነው ሐኪሙ ጨጉዋራ ነው ያለው አሉ፡፡
ሌሎቹ ደግሞ…ልጁ ሕጻን ስለሆነና በትክክል ስሜቱን መግለጽ ስለማይችል ሐኪሙ ሊሳሳት ይችላል፡፡ ይህ ደግሞ የሚያጋጥም ነገር ነው የሚል ነበር መልሳቸው፡፡
አልፎ አልፎ ግን አ..አ…ይ፡፡ ቢሆንም …ሐኪሙ  አስቀድሞ ከመወሰኑ በፊት መጠራጠርና በተገቢው መንገድ ምርመራ እንዲካሄድ ማድረግ ነበረበት ያሉም አሉ፡፡
እንግዲህ በእንዲህ ያለው አጋጣሚ እድል ካልቀናና ተገቢው ሐኪም ካልተገኘ የስንት ሰው ሕይወት እንደሚቀጠፍ መገመት ይቻላል፡፡ የህክምና ስህተት ማለት እንደሌሎች የስራ ዘርፎች ስህተት በቀላሉ ሊተካ ወይንም ሊታረም የማይችል የሰው ሕይወት ጉዳይ ነው። የአንድ ሰው ሕይወት ካለፈ በሌላ ሊተካ አይችልም። ሐኪሙ ቢከሰስ ቢወቀስ እንኩዋን ያ ያለፈ ሕይወት ሊመለስ አይችልም፡፡ አበቃ፡፡ ስለዚህ ይህ ነገር በደንብ ቢታሰብበት ጥሩ ይመስለኛል፡፡ የህክምና ባለ ሙያው በደንብ እውቀቱን ቢያደረጅ እንዲሁም አገልግሎት መስጫ ተቋማቱ በደንብ ቢጠናከሩ እና የአሰራር ዘዴያቸው ግልጽ እንዲሆን አስቀድሞ መሰራት ያለበት ነገር ቢሰራ ለአገልጋዩም ለተገልጋዩም ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡
የታማሚው አባት
አቶ አበበ አሳመረ እንደሚገልጹት በቅድሚያ የሙያ ኃላፊነት የሚባለውን ነገር ስንመለከት ማስረጃው ተቀባይነት አለው ወይ? ከየት ነው መምጣት ያለበት? ማንነው ይህንን ማስረጃ ለመስጠት በሕግ ስልጣን ያለው? …ወዘተ የሚል የማስረጃ ሕግ ስለሌለን ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን ክርክር እያየ ማስረጃ እየመዘነ ውሳኔ እየሰጠ ይገኛል፡፡ ወደፊት ግን መጀመር ያለበት አሰራር አለ፡፡ …ለምሳሌ በሌሎች አገሮች የሙያ ማህበራት አንዱ ሚናቸውና ኃላፊነታቸው የሙያ ኃላፊነት ላይ የሚወሰኑ ውሳኔዎችን ማስተቸት ነው፡፡ ይህም …
በስራ ላይ ያለው ሕግ የጎደለው ነገር ካለ እንዲመለከቱትና እንዲሻሻል ጥያቄ ለማቅረብ ይረዳል፡፡
የማህበር አባላትን በጉዳዩ ላይ ግንዛቤ እንዲያገኙና በአሰራራቸው እንዲጠነቀቁ እንዲሁም ትምህርት እንዲያገኙ ለማድረግ ይረዳል፡፡
ፍርድ ቤቶች በተመሳሳይ ጉዳይ የሚቀርብላቸውን የኃላፊነት መጉዋደል በሚመለከት ቀደም ብሎ የተሰራውን ስራ ወይንም የተወሰነውን ውሳኔ ሲያዩ የህጉን አተረጉዋጎም፣ የማስረጃ አሰባሰብ እንዲሁም እንዴት እንደተመዘነ በሚመለከት ሁሉ የተኬደበትን አሰራር ለማጤንና ለማገናዘብ እንዲረዳቸው ያግዛል፡፡
ከሕክምና አገልግሎት ጋር በተያያዘ የህግ ስራ ለሚሰሩ ማንኛቸውም አካላት ፣ለፖሊሲ አውጭዎች አሰራር ይረዳል፡፡
ከዚህ ውጭ ግን ልንመለከተው የሚገባን ነገር አለ ብለዋል አቶ አበበ፡፡ በሕክምና ሙያ ብቻ ሳይሆን በሌሎች ዘርፎችም ላይ የመገናኛ ብዙሀን የሚያደርሱት የተጋነነ የመረጃ አሰጣጥ በሙያው የተሰማራውንም ሌላውንም ተገልጋይ እኩል የሚጎዳበት ሁኔታ ይስተዋላል፡፡ ለምሳሌ ያህል የሚከተለውን ገጠመኝ ላስታውስ ብለዋል የህግ ባለሙያው አቶ አበበ አሳመረ፡፡
‹…በአንድ ወቅት ከአንዲት ታካሚ ሆድ ውስጥ የፈሳሽ ማምጠጫው ፋሻ ወይንም ጎዝ ተረሳ፡፡ ወደህግ ሲቀርቡ ሶስቱም ሐኪሞች ጥፋተኛ ነን አሉ፡፡ ነገር ግን አለቃቸው በሰጠችው አስተያየት የባለሙያ እጥረት ፣የተቋማቱ የአደረጃጀት አለመሟላት የመሳሰ ሉት ሁሉ አብረው መታየት እንዳለባቸው ነው፡፡ አንድ ሐኪም መስራት ከሚገባው ሰአት በላይ እንዲሰራ ሲገደድ እንደሰው መድከምና መሳት ሊገጥመው ይችላል፡፡ ይህ ለምን ይደረጋል እንዳይባል …ታካሚው ቁጥሩ ከሐኪሙ በላይ ስለሆነ እና በወቅቱ ካልተሰራለት ሊሞት ስለሚችል ቢያንስ እንደምንም ይታይ የሚል ውሳኔም፣ ስምምነ ትም ተደርጎ ሐኪሙ በቅንነት እንዲያየው የተቻለው ሁሉ ይደረጋል፡፡ በዚህ መሀል አንድ ሐኪም አብዛኛውን ሰው አድኖ ግን አንድ ሰው ቢሞትበት ለፍርድ ከመቅረብ ባሻገርም በመገናኛ ብዙሀን በተጋነነ ሁኔታ ለህዝብ አቅርቦ ማሳጣት ሚዛኑን አያጣም ወይ? በሕግ ከሚችለው በላይ በከበደ መልኩ የሚዳኝና በመገናኛ ብዙሀኑም ብዙ የሚባል ከሆነ አንድ ሐኪም እኔ መስራት የሚገባኝ በቀን ይህን ያህል ታካሚ ማየት ብቻ ነው፡፡ ከዚህ በላይ አልችልም ብሎ ጋዋኑን አስቀምጦ ቢወጣ እስትሬቸር ላይ የሚሞተው ሰው ቁጥር ይጨምራል፡፡ የሚል ነበር፡፡
አቶ አበበ እንደሚሉት አንድ የህክምና አሰጣጥ ስህተት ተፈጠረ ሲባል ነገሩን ከብዙ አቅጣጫ መመልከትና መመርመር ይገባል፡፡ የትጋ ነው ስህተቱ የተፈጠረው? በባለሙያው ግድየለሽነት ወይንም የእውቀት ማነስ ነው? ወይንስ በተቋሙ የአሰራር ዘዴ መበላሸት ነው? …ወዘተ ይህንን ለማረጋገጥ የሰከነ አካሄድን ይጠይቃል፡፡ ካለበለዚያ ግን የህክምና ባለሙያው አስቀድሞውኑም ትምህርቱን ወይንም ሙያውን እንዳይመርጠው እስከማድረግ ድረስ የሚያደርስ የተሳሳተ አካሄድ ሊፈጠር ስለሚችል መጠንቀቅ ይፈልጋል፡፡ እንደ አቶ አበበ ማብራሪያ በኢትዮጵያ የግልም ሆነ የመንግስት አንድም ሆስፒታል ደረጃውን መቶ በመቶ ባሙዋላ መልኩ የተደራጀ አይደለም፡፡
በሌሎች አገሮች የተደረጉ ጥናቶች እንደሚያመለክቱት በሕክምና ተቋማት አደረጃጀት አለመስተካከልም ይሁን በባለሙያው አሰራር ስህተት ምክንያት በሚፈጠሩ ስህተቶች የተነሳ በሕክምና ባለሙያውና በታካሚው መካከል የሚፈጠሩ ቅርበቶች ሊሻክሩ ይችላሉ፡፡ ሐኪሙም ሁልጊዜ ኃላፊነትን የሚያስብ ከሆነ በቀጥታ በትክክል ሊያድን የሚችለውን መድሀኒት ከማዘዝ ይልቅ መጠራጠርን በማብዛት በኃላፊነት ላለመጠየቅ ሲባል …ይህ ቢሆንስ…ይህ ባይሆንስ ስለሚል የተለያዩ ላቦራቶሪዎች ውጤት እንዲቀርብለት ማዘዝ የመሳሰሉትን እርምጃዎችን ሊወስድ ይችላል፡፡ ይህ አካሄድ ደግሞ ሕመምተኛው አፋጣኝ ውሳኔን እንዳያገኝ …እንዲሁም ለተለያዩ ወጪዎችም ሊዳረግ ይችላል፡፡
አቶ አበበ አሳመረ በማጠቃለያቸው የተናገሩት ‹‹…ሐኪሞች ሳይጨነቁና ሳይፈሩ በራስ በመተማመን የሚሰሩ ከሆነ ተገልጋዩም በደንብ ይጠቀማል፡፡ ስለሆነም በኃላፊነት የሚጠየቁ ባለሙያዎች የሚከፍሉት ካሳ የተጋነነ እና ሕይወትን የሚፈታተን መሆን የለበትም። ሆን ተብሎ የተፈጸመ ጥፋት ካልሆነ በቀር ወደወንጀል ኃላፊነት መውሰድም ባይኖር ጥሩ ነው፡፡ ባጠቃላይም ማህበራቱ ተጠናክረው ሌላው አለም እንደሚንቀሳቀሰው ቢንቀሳቀሱ እንዲሁም በዘርፉ የተለያዩ ጥናቶች ማለትም ከኢንሹራንስ ከሕግ አሰራር የመሳሰሉት ሁሉ መሰረት ተደርገው ጥናቶች ቢካሄዱ በቀጣይ ለሚኖረው አሰራር ይጠቅማል፡፡›› ብለዋል፡፡ 

የሩስያ መከላከያ ሚኒስቴር፣ የአገሪቱ የጦር ሃይል አባላትና ወታደሮች ፌስቡክን ጨምሮ በተለያዩ ማህበራዊ ድረገጾች ላይ ፎቶ ግራፋቸውንና ሌሎች ጽሁፎቻቸውን እንዳይለጥፉ የሚከለክል ህግ እያወጣ መሆኑን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ሚኒስቴሩ ይህንን ህግ ለማውጣት ያነሳሳው፣የደህንነትና የመረጃ ማፈትለክ ስጋት እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፤ ወታደሮቹ የሚለጥፏቸው ፎቶ ግራፎችና ሌሎች ጽሁፎች የት አካባቢና የትኛው የጦር ሰፈር ላይ እንደሚገኙ ለጠላት ሃይል ወታደራዊ መረጃ ሊሰጡ ይችላሉ መባሉን አመልክቷል፡፡ ህጉ ከመጪው ጥር ወር ጀምሮ ተግባራዊ
ይሆናል ተብሎ እንደሚጠበቅም የጠቆመው ዘገባው፤ የዩክሬን መከላከያ ሚኒስቴርም በ2015 ላይ በተመሳሳይ ሁኔታ አብዝተው ማህበራዊ
ድረገጽ በሚጠቀሙ ወታደሮቹ ጉዳይ ከፍተኛ ስጋት ውስጥ ገብቶ እንደነበር አስታውሷል፡፡


የኖቤል የሽልማት ተቋም የ2017 የኖቤል አሸናፊዎችን ዝርዝር ከያዝነው ሳምንት መጀመሪያ አንስቶ ይፋ በማድረግ ላይ ሲሆን፣ እስካሁንም የፊዚክስ፣ የኬሚስትሪ፣ የህክምና እና የስነጽሁፍ ዘርፍ ተሸላሚዎች ታውቀዋል፡፡
ተቋሙ ባለፈው ሰኞ ይፋ ባደረገው ቀዳሚው የዓመቱ የኖቤል የህክምና ዘርፍ ተሸላሚዎች ዝርዝር፣ ሰርካዲያን ሪትም በተባለ የዘርፉ ምርምር የላቀ ፈጠራ ያበረከቱት ሶስቱ አሜሪካውያን ተመራማሪዎች፡-  ጄፍሪ ሲ ሃል፣ ማይክል ሮስባሽ እና ማይክል ደብሊው ያንግ አሸናፊዎች መሆናቸውን አስታውቋል፡፡
ማክሰኞ ዕለት ይፋ የተደረገው የፊዚክስ ዘርፍ ተሸላሚዎች ዝርዝር በበኩሉ፡- ሌዘር ኢንተርፌርኖሜትር ግራቬቲሽናል ዌቭ በተባለው የፊዚክስ መስክ የላቀ የምርምር ውጤት ያበረከቱት ጀርመናዊው ሬነር ዌስ እና አሜሪካውያኑ ተመራማሪዎች ባሪ ሲ ባሪሽ እና ኪፕስ ኤስ ትሮን የዘርፉ አሸናፊዎች እንደሆኑ አስታውቋል፡፡
ሬነር ዌስ የ1 ሚሊዮን ዶላር ሽልማቱን ግማሽ ሲወስድ፣ ሌሎቹ ሁለት ተመራማሪዎች ቀሪውን ገንዘብ እኩል እንደሚካፈሉ ተቋሙ አስታውቋል፡፡
የዓመቱ የኖቤል የኬሚስትሪ ዘርፍ ተሸላሚዎችን ባለፈው ረቡዕ ይፋ ያደረገው ዘ ሮያል ስዊድሽ አካዳሚ ኦፍ ሳይንስስ፣ እጅግ ረቂቅ የሆኑ ደቂቀ አካላትን በከፍተኛ ሁኔታ አጉልቶ የሚያሳይ ማይክሮስኮፕ የፈጠሩትና የባዮ ኬሚስትሪ መስክ ምርምርን ወደላቀ ደረጃ ያሳደገ ነው የተባለለት የዚህ የፈጠራ ውጤት ባለቤቶች የሆኑት ስዊዘርላንዳዊው ጃክ ዶቼት፣ እንግሊዛዊው ሪቻርድ ሄንደርሰን እና አሜሪካዊው ጆኣኪም ፍራንክ የዘርፉ አሸናፊዎች መሆናቸውን አስታውቋል፡፡  
“ዘ ሪሜንስ ኦፍ ዘ ዴይ” እና “ኔቨር ሌት ሚ ጎ” በሚሉት ተወዳጅ ልቦለድ መጽሐፍቱ የሚታወቀው እንግሊዛዊው ደራሲ ኢካዙኦ ሺጉሮ፤ 830 ሺህ የእንግሊዝ ፓውንድ የሚያስገኘው የዘንድሮ የኖቤል የስነ ጽሁፍ ዘርፍ ተሸላሚ መሆኑን ተቋሙ ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
እ.ኤ.አ በ1954 በጃፓኗ ናጋሳኪ የተወለደው ደራሲው፣በረቀቀና ጥልቅ ስሜትን በሚጭር አጻጻፉ ዓለማቀፍ ዝናን እንዳተረፈ ያስታወቀው ተቋሙ፤ ሁለቱ ተወዳጅ ስራዎቹ በፊልም መልክ ተሰርተው ለእይታ መብቃታቸውን ተከትሎም ዝናው የበለጠ በዓለም ዙሪያ መናኘቱን አመልክቷል።
የአልፍሬድ ኖቤል መታሰቢያ የሆነው የኢኮኖሚክስ ዘርፍ የ2017 ተሸላሚ በበኩሉ፤ ከነገ በስቲያ ስቶክሆልም ውስጥ በሚከናወን ስነስርዓት በይፋ እንደሚገለጽ ይጠበቃል፡፡

“ት/ቤቶቹ በራሳቸው ስልጣን የዋጋ ጭማሪ ማድረግ አይችሉም”

በዘንድሮው ዓመት በአንዳንድ የግል ት/ቤቶች የተደረገው የክፍያ ጭማሪ ከአቅማቸው በላይ እንደሆነ የገለፁ ወላጆች፤ ጭማሪው ልጆቻቸውን በግል ት/ቤቶች ለማስተማር እንዳይችሉ የሚያደርግ መሆኑን ተናገሩ፡፡ ት/ቤቶቹ በራሳቸው ፍቃድና ፍላጎት በየጊዜው በክፍያ ላይ የሚያደርጉት ከፍተኛ የዋጋ ጭማሪ አቅማቸውን የሚፈታተንና የአገሪቱን ነባራዊ ሁኔታ ያላገናዘበ መሆኑን ወላጆች ጠቁመዋል፡፡ የአዲስ አበባ ት/ቢሮ በበኩሉ፤ት/ቤቶቹ በራሳቸው ስልጣንና ፍላጎት ብቻ የዋጋ ጭማሪ ለማድረግ እንደማይችሉና ጭማሪ ለማድረግ ሲፈልጉ፣ ጭማሪውን ለማድረግ ያስገደዳቸውን በቂ ምክንያት በመዘርዘር፣ ለኤጀንሲው አቅርበው፣ ኤጀንሲው በጉዳዩ ላይ ከት/ቤቶቹ ባለቤቶችና ከወላጅ ኮሚቴዎች ጋር በሚደረግ ውይይት የሚወሰን መሆኑን ገልጿል፡፡
ሁለት ህፃናት ልጆቻቸውን በአንድ የግል ት/ቤት ውስጥ ላለፉት አራት አመታት ማስተማራቸውን የሚናገሩ አቶ ሰለሞን ታየ የተባሉ ወላጅ፤ “በዘንድሮው ዓመት የተደረገው 80 ፐርሰንት ጭማሪ ከአቅሜ በላይ በመሆኑ ልጆቼን ከት/ቤቱ ለማስወጣትና በመንግስት ትምህርት ቤት ለማስገባት ተገድጃለሁ፤” ብለዋል፡፡
 የክፍያ ጭማሪውን በተመለከተ አስቀድሞ የተነገራቸው ነገር አለመኖሩን የሚገልፁት እኚሁ ወላጅ፤ ት/ቤቶቹ ትምህርት የሚጀመርበት ጊዜ ሲቃረብና በሌሎች ት/ቤቶች ምዝገባ ሲጠናቀቅ የክፍያ ጭማሪ ማድረጋቸውን የሚያሳውቁት፣ ወላጆች ልጆቻቸውን የሚወስዱበት ሌላ ቦታ ስለማይኖር የዋጋ ጭማሪውን በግዳቸው ይቀበላሉ ከሚል መነሻ ነው ይላሉ፡፡ ቤተ ክህነት በምታስተዳድረው ት/ቤት ልጆቻቸውን  እንደሚያስተምሩ የገለፁልን  ሌላ ወላጅ ደግሞ፣ ት/ቤቱ በየጊዜው በዘፈቀደ የሚያደርገው የዋጋ ጭማሪ በእጅጉ እንዳማረራቸውና ለሚያቀርቡት አቤቱታ ምላሽ የሚሰጣቸው አካል በማጣታቸው ተስፋ መቁረጣቸውን ገልፀዋል፡፡
ት/ቤቶቹ በየጊዜው ከሚያደርጉት የዋጋ ጭማሪ በላይ እጅግ ያማረራቸው “የትምህርት መርጃ መሳሪያዎች”  እየተባሉ ለት/ቤቱ ገቢ እንዲያደርጉ የሚጠየቋቸው እንደ ሶፍት፣ ሳሙና፣ ደስታ ወረቀት፣ ደርዘን እስኪርብቶና እርሳስ የመሳሰሉት መሆናቸውን ወላጆች ይጠቅሳሉ። “ጉዳዩ ተመልካችና ሃይ ባይ በማጣቱ፣ ት/ቤቶቹ እንደፈለጋቸው ይጫወቱብናል፤” ሲሉም ያማርራሉ። በጉዳዩ ላይ ማብራሪያ እንዲሰጡን የጠየቅናቸው አንዳንድ የግል ት/ቤት የሥራ ኃላፊዎች፤ ማነጋገር ያለብን የት/ቤት ባለቤቶቹን እንደሆነ ገልፀውልናል - እነሱ ተቀጥረው የሚሰሩ በመሆናቸው ምላሽ ለመስጠት እንደማይችሉ በመጠቆም፡፡ ሆኖም የት/ቤቶቹን ባለቤቶች ለማግኘት ያደረግነው ሙከራም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡
የአዲስ አበባ ት/ቢሮ ምክትል የቢሮ ኃላፊ አቶ ኃይለስላሴ ፍስሃ በበኩላቸው፤ ት/ቤቶቹ በራሳቸው ፍቃድና ፍላጎት በየጊዜው የዋጋ ጭማሪ ማድረግ እንደማይችሉና ጭማሪውን ለማድረግ የተገደዱበትን ምክንያት በዝርዝር ለኤጀንሲው የማቅረብ ግዴታ እንዳለባቸው ገልፀዋል፡፡ ኤጀንሲው ከት/ቤቶቹ ባለቤቶች ጋር ውይይት ካደረገ በኋላ ት/ቤቶቹ ከወላጅ ኮሚቴ ጋር ተወያይተውና በጭማሪው መጠን ላይ ስምምነት ላይ ደርሰው፣ ጭማሪ ማድረግ እንደሚችሉ አስረድተዋል፡፡ በሚቀጥለው ዓመት የሚያደርጉትን የክፍያ ጭማሪም የትምህርት ዘመኑ ከመጠናቀቁ 3 ወር በፊት፣ በቀጣዩ ዓመት ጭማሪ የሚያደርጉ መሆኑን ከነጭማሪው መጠን ገልፀው የማሳወቅ ግዴታ እንዳለባቸው ኃላፊው ተናግረዋል። ከዚህ አሠራር ውጪ የሚደረገው ጭማሪ ግን ህገ ወጥ እንደሆነና ቅሬታ ያላቸው ወላጆች፣ በየደረጃው ለሚገኙ የት/ቢሮዎች በማሳወቅ፣ በህገወጦች ላይ እርምጃ ማስወሰድ እንደሚችሉ አቶ ኃይለሥላሴ ፍስሃ ገልፀዋል፡፡


በህዝብ የተመረጡ የኪነጥበብ ሥራዎች ይሸለማሉ

      በዛሚ 90.7 ኤፍኤም፣ በ2001 ዓ.ም የተጀመረውና በህዝብ ምርጥ የተባሉ የኪነጥበብ ሥራዎችንና ሙያተኞችን በየዓመቱ የሚሸልመው “8ኛው አዲስ ሚዩዚክ አዋርድ” ጥቅምት 6 ቀን 2010 ዓ.ም ከቀኑ 11፡00 ሰዓት ጀምሮ በሐርመኒ ሆቴል ይካሄዳል፡ ፡ በስምንት ዘርፎች የኪነ ጥበብ ሥራዎችን በህዝብ ምርጫ አወዳድሮ አሸናፊዎችን የሚሸልመው “አዲስ ሚዩዚክ አዋርድ”፤ የዘንድሮውን ለየት የሚያደርገው በጄቲቪ ኢትዮጵያም መጀመሩ እንደሆነ የፕሮግራሙ አዘጋጅ ይገረም ስንታየሁ (ዲጄ ቤቢ) ገልጿል፡፡ሽልማቱም “የዓመቱ ምርጥ አልበም”፣ “ምርጥ ነጠላ
ዜማ”፣ “ምርጥ የሙዚቃ ቪዲዮ”፣ “ምርጥ አዲስ ድምፃዊ”፣ “ምርጥ የሙዚቃ አቀናባሪ”፣ “ምርጥ ፊልም”፣ “ምርጥ ተዋናይ” እና “ምርጥ ተዋናይት”
በሚሉ ስምንት ዘርፎች አሸናፊዎችን የሚሸልም ሲሆን “የኪነ ጥበብ ባለውለታ” በሚል ልዩ ተሸላሚ እንደሚኖርም የሽልማቱ አዘጋጅ ዲጄ ቤቢ ጨምሮ ገልጿል፡፡በእለቱ ሁለት ትልልቅ የሙዚቃ ባንዶች ከታዋቂ ድምፃውያን ጋር የሙዚቃ ስራቸውን እንደሚያቀርቡ የጠቆመው ዲጄ ቤቢ፤ በፕሮግራሙ ላይ መታደም የሚቻለው በግብዣ ካርድ እንጂ የመግቢያ ትኬት እንደማይሸጥ በመጠቆም፣ ሰዎች ተጭበርብረው እንዳይገዙም አሳስቧል፡፡

በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ የግጥሞችና የአጫጭር ልቦለዶችን ስብስብ ያካተተው የደራሲ አማን እንድሪስ “የግዜሩ ቀን”የተሰኘ መፅሐፍ፣ ነገ ከረፋዱ 4፡00 ሰዓት ጀምሮ በሀገር ፍቅር ቴአትር አዳራሽ ይመረቃል፡፡ከምረቃው በተጨማሪ በመፅሐፉ ላይ ዳሰሳ የሚደረግ ሲሆን ገጣሚያኑ ከፈለኝ ባዘዘው፣በላይ በቀለ ወያ፣ ሚካኤል ምናሴ፣ መኳንንት መንግስቱና ዶ/ር ሀብታሙ ፍቃዱ ከመፅሐፉ የተመረጡ ግጥሞችንና የራሳቸውን ስራዎች ለታዳሚያን እንደሚያቀርቡ ተገልጿል፡፡ በ119 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፉ፤ በ41 ብር ከ80 ሳንቲም እየተሸጠ ነው፡፡

ተርጓሚ ሕይወት ታደሰ፤ የሐማ ቱማን The Case of the Socialist Witchdoctor “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ” በሚል ወደ አማርኛ የተረጎመች ሲሆን የሕይወት ተፈራን Mine to Win ደግሞ “ኃሰሳ” በማለት ወደ አማርኛ መልሳዋለች፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በህግ ሙያ በመጀመሪያ ድግሪ የተመረቀችው ሕይወት ታደሰ፤ እንዴት ወደ ትርጉም ሥራ ልትገባ ቻለች? የተርጓሚነት ተሞክሮዋስ ምን ይመስላል? ”አንደምታ” ከተሰኘው ድረገፅ ላይ ያገኘነውን ቃለምልልስ ለጋዜጣ እንዲመች አድርገን እንዲህ አቅርበነዋል፡፡ ከልጅነት እስከ ዕውቀት --- ትናገራለች፡፡ ወደፊት ልትስራ ያቀደቻቸውንም እንዲሁ፡፡የህግ ምሩቋን ተርጓሚ ሕይወት ታደሰን እነሆ፡፡ አንብቧት፡፡


እስቲ በልጅነትሽ ከመጻህፍት ጋር ባለሽ ትውውቅ ጨዋታችንን እንጀምር ---
በልጅነቴ መጀመሪያ ላይ ያነበብኳቸው የልጆች መጻሕፍት አልነበሩም። በስምንት ወይም በዘጠኝ አመቴ ያነበብኩትን የመጀመሪያ መጽሐፍ (“ግርዶሽ” በሲሳይ ንጉሡ) ጨምሮ በዚያን ጊዜ አካባቢና ከዚያ በኋላ ሁሉ ይታተሙ የነበሩትን ያካትታል። ቤታችን ውስጥ በርካታ ልብወለድ፣ የታሪክና ጥቂት የሚባሉ ከዚህ ውጪ የሆኑ መጻሕፍት ነበሩ። ልብወለዶቹ የሀገር ውስጥ ወጥ ስራዎች፣ ብዛት ያላቸው ትርጉሞችና ጥቂት በእንግሊዘኛ የተጻፉ ናቸው። በሀገራችን ታሪክ ዙሪያ በተለያየ ጊዜ የተጻፉ መጻህፍትም ቤት ውስጥ ነበሩ። እንዲሁም በይዘታቸው ለየት ያሉ በዚያ እድሜዬ የሚገርሙኝ አንዳንድ መጻሕፍት ነበሩበት፡፡ በቤት ውስጥ የህክምና እርዳታ አሰጣጥ ላይ የሚያተኩር ወደል የእንግሊዘኛ መጽሐፍና ‘ባሃኡላህና አዲሱ ዘመን’ የሚል አንድ ደቃቃ መጽሐፍ ለአብነት ያህል ትዝ ይሉኛል። በትምህርት ቤት ደግሞ እንደው ለይስሙላ በክፍል ውስጥ ይሰጡ የነበሩ እንደ ‘እጅ ስራ’ ያሉ የትምህርት ክፍለ ጊዜዎች ላይ የልጆች መጻሕፍትን የምታነብልን ታሪክ የምትባል መምህርት ነበረች። ለኔ ባለውለታዬ ናት። ‘የተኛችው ቆንጆ፣ ሲንደሬላ፣ አንድ ሺህ አንድ ሌሊት፣ ቲሙርና ቡድኑ ወዘተ’ በሙሉ መኖራቸውን ያወቅሁት በእሷ ምክንያት ነው። ብዙዎቹ እነዚህ መጻሕፍት ትርጉሞች ናቸው። ከትምህርት ቤት ተመልሼ ማታ ማታ እነዚያን ታሪኮች ለእህቶቼና ለእናቴ ስተርክ አመሻለሁ። ሳላስብበት ትረካን (story telling) ወደድኩ።
ቤት ውስጥ የነበሩትን ልብወለዶች በተለይ ትርጉሞቹን በሙሉ አንብቤያቸዋለሁ። ኢንተርኔት፣ ጉግል የመሳሰለውን በማላውቅበት፣ ለአቅመ የብእር ጓደኛ ባልበቃሁበት እድሜ ላይ ስለነበር ያነበብኳቸው፣ በርካታ አስደናቂ ዓለማትን ለምናቤ ከፍተዋል። ከ1983 ወዲህ ደግሞ ከዚያ በፊት ያለፈውን የአስራ ሰባት አመት ታሪክ በተለያየ አኳኋን የሚዘክሩ መጻሕፍት መጡና ቀልቤን ማረኩት። ከዚህ በኋላም እናቴ የBritish Council ቤተመጻሕፍት የአባልነት መታወቂያ አወጣችና፣ የተለያዩ የእንግሊዘኛ መጻሕፍትን አስነበበችኝ፡፡ አባቴም የእንግሊዝ ሥነጽሑፍ ቁንጮ ደራሲያንን ዘመን ተሻጋሪ ሥራዎች፣ ለታዳጊ ወጣቶች እንዲሆኑ አጠር ተደርገው የተዘጋጁትን፣ ከፍ ስንልም እንደዚያው ጠንከር ያሉ መጻሕፍትን ገዝቶ ያስነብበን ነበር።
የንባብ ባህሉ በትምህርት ቤትም ቀጠለ ወይስ ---?
እስከ ስምንተኛ ክፍል በተማርኩበት የገዳመ ሲታውያን ማርያም ጽዮን ትምህርት ቤት (Cistercian Monastery Mariam Tsion School) የማስታውሰው፣ የተለመደው የአማርኛ ቋንቋችንን የማዳበሪያ ተግባራት ይሰጡን እንደነበረ ነው፤ ግጥም መጻፍ፣ ክርክር ማድረግ የመሳሰሉት። ሰባተኛና ስምንተኛ ክፍል ላይ ግን የአማርኛ መምህራችን ከዚህ በላይ ገፍቶ ያተጋን ነበር። ተውኔት ደርሰንና አዘጋጅተን፣ በክፍል ውስጥ ስናቀርብ አስታውሳለሁ። በአማርኛ ሥነጽሑፍ ውስጥ እስካሁንም የሚጠቀሱ አውራ ደራስያንና ስራዎቻቸው ላይ ሂሳዊ ንባብ እንዲሁም ግምገማዎችንም እንድናካሂድ ያደርገን ነበር። በዚህ መልኩ መምህራችን (አቶ ታሪኩ)፤ የአማርኛ ሥነጽሑፍን እንደው ዝም ብሎ ማንበብ ብቻ ሳይሆን ማጣጣምንም አስተምሮናል።የሁለተኛ ደረጃ ትምህርትን በተከታተልኩበት ሰላም የሕጻናት መንደር ትምህርት ቤት ደግሞ መደበኛ የመማሪያ መጽሐፉ ከሚጠቁመው በተጨማሪ ለማትሪክ የበለጠ ዝግጁ ያደርጋል ብለው ያሰቡትን ይዘት አክለው የሚያስተምሩን ሁለት የአማርኛ መምህራን ነበሩ። ስለዚህ ከተማርነው ይዘት ፈሊጣዊ አነጋገሩ፣ ቅኔው፣ ምሳሌያዊ አነጋገሩና ይህን የመሳሰለው ይበዛ ነበር። እና ደግሞ ቁጥር የለሽ (መምህራኑ ‘ጥሬ’ የአማርኛ ቃላት የሚሏቸው) በተለምዶ በሚነገረው አማርኛችን ውስጥ እምብዛም የማንገለገልባቸው አስገራሚ ቃላትን አጥንተናል።
ድራማና ጭውውት ደርሶ አዘጋጅቶ መተወን፣ በክፍል ውስጥ ብቻ  ሳይሆን፣ በክፍሎች መካከል በውድድር መልክ የሚካሄድና፣ በየማለዳው ቀኑን በጸሎት በምንጀምርበት አዳራሽ (ቻፕል) ውስጥ ለተማሪዎችና ወላጆች በሚቀርቡ ዝግጅቶችም ላይ የምንሳተፍበት ሁኔታ ነበር።
እንዴት ነው ሕግን ለማጥናት የወሰንሽው?
ወፍራም እንጀራ ያወጣል፣ ያስተማምናል ስለተባልኩና፣ የተባልኩትን ስለሰማሁ! ጉጉት፣ ጥያቄ፣ ቀጥታ ንግግርና ትንሽ ድፍረት የምታሳይ፣ በትምህርት ቤት ደህና ውጤት ያላት ታዳጊ ስትሆን ጸሐፊ ወይም ተዋናይት መሆን ትችላለች ብሎ  የሚመኝልህ ብዙ ሰው አይኖርም፤ ነገረ ፈጅ እንጂ! ዩኒቨርሲቲ ስገባ  ምን ማጥናት እንዳለብኝ ብዙዎችን ሳማክር ተመሳሳይ ምላሽ ስላገኘሁ፣ ይህንኑ በመከተል ሕግን መረጥኩ። 
በአገራችን በሕግ ሙያ የተመረቁ  በርካታ የኪነጥበብ ዝንባሌ ያላቸው ሰዎች አሉ፡፡ የተለየ ምክንያት ያለው ይመስልሻል?
እውነት ነው። ሕግ ተምረው የኪነጥበብ ዝንባሌ  ያላቸው ምሩቃን ጥቂት አይደሉም። በተለይ ከመነሻው ትንሽም ቢሆን ኪነጥበባዊ ፍላጎት (interest) የነበራቸው ሰዎች ከሆኑ። ምክንያቱ ምን እንደሆነ ሳስብ የሚከተለው ይታየኛል፤ በተለይ በራሴው ልምድ ከተገነዘብኩት በመነሳት። አንደኛ የሕግ ትምህርት የቋንቋና የግንዛቤ ክህሎትን ይሞርዳል ብዬ አስባለሁ። የሕግ ትምህርት የግድ ከባድ አይደለም፤ ግን እጅግ ሰፊ ነው። የሚነበበው ብዙ ነው፣ የሚተነተነው ብዙ ነው፣ የሚጻፈው ብዙ ነው። የምታነባቸው መጻሕፍት አይነትና ብዛት ቋንቋህና እውቀት አዘል ግንዛቤህ ላይ አይነተኛ ተጽዕኖ  አላቸው። በትምህርት እንዲሁም በስራ ወቅት እንድታዘጋጃቸው የሚጠበቁብህ የጽሑፍ አይነቶች የመተንተን፣ የማሰናሰልና የማስረዳት ክህሎትህ ላይ እንዲሁ ተጽዕኖ አላቸው።
ሁለተኛ ሕግ ራሱ ሁሉን ጠለቅ (pervasive) ባሕሪይ አለው። ሕግ የማይመለከተው ወይም የማይገዛው የሕይወታችን ክፍል የለም። ሕግ የሚባለው ምን እንደሆነና እንደምን እንደመጣ ለመረዳት መጀመሪያ ላይ የፍልስፍና ትምህርት፣ በመቀጠል የሕግ ፍልስፍና ትምህርት ስትወስድ ዘላለማዊ የሚባሉትን የሰው ልጅ ኀሠሣዎች ገረፍ አድርገህ ታልፋለህ። ከዚያ በኋላ በሕግ ግምትና  በሕግ አተያይ ሰው ከመሆን አንስቶ፣ የግለሰብን ሕይወትና ከግለሰብ፣ ከማህበረሰብና  ከመንግስት ጋር የሚኖር መስተጋብር፣ የሀገር እና የአለም አቀፍ ህብረተሰብን መስተጋብር፣ በየፈርጁ የሚፈትሹ ሃሳቦችን፣ የሚገዙ መርሆችን ታያለህ። በአጭሩ ሕግ መቼ ተፀነስክ ከሚለው የማህፀን ውስጥ ሀቅ ጀምሮ ቤትህን፣ ምድርን፣ ባህርን፣ አየርንና አሁን ደግሞ ‘ቨርቹዋል’ የምንለውንም አለም እንዲሁም እዚህ ሁሉ ውስጥ ያለውን ክንውን ይቃኛል። ኪነትስ? በአንዳች አይነት መልኩ ይህንኑ አታደርግም?
የኔ ፍላጎት ሥነጽሑፍና ቴአትር ስለነበር፣ አባቴ አበበ ባልቻን ምሳሌ አድርጎ፣ ሕግ ትምህርት ቤት እንድገባ አሳመነኝ። እኔ አብዛኛዎቹን አመታት ክፍል ውስጥ ግጥም እየጻፍኩ አሳለፍኳቸው። ቴዎድሮስ ሞሲሳ ዘፈን ሲያወጣ፣ ጓደኞቼ ‘የሒዊ መጨረሻ’ ብለው ለወራት ተዝናኑብኝ።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ  የነበረው ኪነጥበባዊ ድባብ ምን ይመስል ነበር?
አአዩ በነበርኩበት ጊዜ፣ እኔና ጓደኞቼ እንሳተፍበት የነበረው የባህል ማእከሉን የግጥም ምሽት ነበር። በሳምንት አንድ ቀን የሚጽፉ ልጆች ግጥሞቻቸውንና ወጎቻቸውን የሚያካፍሉበት መድረክ ነው። በወቅቱ የነበረው የመብራት መጥፋት ወረፋ እንኳን ሳያግደው በመማሪያ  ክፍሎች ውስጥ በሻማ  ብርሃን ይከናወን ነበር። በ1993 በዩኒቨርሲቲው ውስጥ በተነሳው ግርግር ምክንያት ተቋረጠ። ከዚያ  በኋላም ተማሪዎች በቡድን ተሰባስበው መገኘት ስለተከለከሉ የሥነጽሁፍ ምሽቱን ማስቀጠል አልተቻለም። ለወትሮውም ቢሆን ከሚቀርቡት ጽሁፎች ውስጥ ጥቂት የማይባሉት ይዘታቸው ፖለቲካዊ እንደሆነ  የታወቀ  ነውና። በ1993 የትምህርት ዘመን የሁለተኛውን ሴሚስተር ተምሮ ላለመጨረስና ፈተና ላለመውሰድ የወሰኑት መደበኛ ተማሪዎች በሙሉ ለአንድ አመት በትምህር  ገበታ ላይ እንዳይገኙ ተደርገው ተቀጡ። በመሆኑም በ1994 እንኳን እንደወትሮው የደመቀ የሥነጽሁፍ ምሽት ሊካሄድ፣ በግቢው ውስጥ የቀሩት እኛ የሕግ ትምህርት ቤት ተማሪዎችና በዚሁ አመት የገቡ አዲስ ተማሪዎች ብቻ ነበሩ። ምናልባት በሌሎች መርሃ ግብሮች የሚማሩ ተማሪዎችም ነበሩ ይሆናል፣ በትክክል አላስታውስም። የማስታውሰው እንደ ድንጋይ የሚካበደውን ጭርታ ብቻ ነው።
በ1995 ተማሪዎች ከተመለሱና  ነገሮች ከተረጋጉ በኋላ ግን እኔና የክፍል ጓደኛዬ የሆነው ይርጋ ገላው (ገጣሚና ደራሲ)፣ የተቋረጠው መድረክ መቀጠል እንዳለበት ስላሰብን፣ በወቅቱ ወደ ነበሩት የዩኒቨርሲቲው ምክትል ፕሬዚደንቶችና ሌሎችም የሚመለከታቸው አካላት በመሄድ የግጥም ምሽቱ በድጋሚ እንዲጀመር ጠየቅን። ግልጽና  ከፍተኛ  ማስጠንቀቂያ ተሰጥቶን ተፈቀደ። መድረኩም በሌሎች እገዛ እንደገና ጀመረ። ልጆች አሁንም ፖለቲካዊ አመለካከታቸውን በስራዎቻቸው መግለጽ አላቆሙም ነበርና ከባህል ማእከሉ ተቆጣጣሪዎች ተግሳጽና ምክር፣ አንዳንዴም የ‘እባካችሁ ሁላችንንም እንዳታሳስሩን’ ልመናን አስተናግደናል።
ከባህል ማእከል ባለፈ ደግሞ ተለቅ ያሉ የሥነጽሁፍ መድረኮችን ከሌሎችም ጓደኞቻችን ጋር በመሆን እናዘጋጅ ነበር። በተለመደው በሳምንት አንዴ  በሚዘጋጀው መድረክ ከሌሎቹ ካምፓሶች የሚመጡት ተማሪዎች ቁጥር እምብዛም ስላልነበረ፣ አልፎ አልፎ እያዘጋጀን ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ፋኩልቲ አዳራሽ የምናቀርበው መድረክ እነዚህንና ሌሎችንም ይስብ ነበር። በስድስት ኪሎና አካባቢው በሚገኙ ትምህርት ቤቶች ከይርጋ ጋር እየተዘዋወርን፣ ትምህርት ቤቶቹ ከተማሪዎቻቸው መካከል መርጠው በእኛ ዝግጅት ላይ ግጥም የሚያነቡ ታዳጊዎችን እንዲልኩልን ስንጠይቅ ሁሉ አስታውሳለሁ።
እኔና ጓደኞቼ እንደሌሎች ብዙዎች ከግጥም ምሽቱ በኋላ የምናዘወትረው ልማድ ነበረን። ተያይዘን ‘አሴ ቤት’ ወይም ‘ማዘር ቤት’ እንሄዳለን። በዚያም ምሽቱን መድረክ ላይ በቀረቡት ስራዎች መንስዔነት የተለያዩ ሃሳቦች ተነስተው ይንሸራሸራሉ። በመሆኑም በተለያዩ ርእሰ ሃሳቦች ላይ በልዩ ሁኔታ ስምም የሆንነውና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተቀራረብን የመጣን ልጆች አንዲት ማኅበር መሰረትን። ማህበሯም በተማሪዎች ዲን ጽ/ቤት እውቅና አግኝታ፣  በግቢው ውስጥ አንዳንድ ዝግጅቶችን በማከናወን መንቀሳቀስ ጀመረች። አላማዋ ለተማሪዎች/ለወጣቶች በሃገር በቀል ባህሎችና ማንነት፣ በአፍሪካዊ ማንነትና ትልሞች እና በመሳሰሉ ጉዳዮች ላይ ግንዛቤ ለመፍጠር ነበር። የክዋሜ ንክሩማ ልጅ ጋማል ንክሩማ ተገኝቶ ለተማሪዎች ንግግር ያደረገበት በማህበሯ የተዘጋጀው መድረክ ከማይረሱኝ አንዱ ነው። በኋላ ላይ የመስራቾች የመመረቂያ ጊዜ እየተቃረበ ሲመጣ፣ ማኅበሯን ከግቢ ውጪ እንደ ድርጅት የማስመዝገብ ሃሳብ መጣ፤ ተመዘገበችም። ከጊዜ በኋላ ነባር መስራቾች በተለያየ የግል ምክንያት ብንጎድልም፣ ከመካከላችን ጎበዛዝትና ምርጦች የሆኑት ግን ይዘዋት፣ ደግፈዋት ቀጥለዋል፤ ዛሬም ድረስ እየሰራች ነው።
የሐማ ቱማን “The Case of the Socialist Witchdoctor” እና የሕይወት ተፈራን “Mine to Win” እንዴት ለመተርጐም ወሰንሽ?
“The Case of the Socialist Witchdoctor” (“የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ”) ጋር የተገናኘሁት በአጋጣሚ ነው። መጽሐፉ በሀገር ውስጥ እንደ ልብ የማይገኝ በመሆኑ ፎቶ ኮፒውን አግኝታ ያነበበች ጓደኛዬ፣ ደጋግማ ስላነሳችብኝ ተውሺያት አነበብኩት። የመጀመሪያውን ክፍል ሙሉ በሙሉ ሳልጨርሰው ለመተርጎም ወሰንኩ፡፡ እንደ ሀገር እንደ ህዝብ ስለራሳችን ያልተቀበልናቸውና ዘወትር ሸፋፍነን የምናልፋቸውን አስቀያሚ ገጽታዎቻችን እንዲሁም እርስ በእርስ የተደራረስነው ግፍ፣ የተገበርነውን ክፋት እያዋዛ ሆጭ አድርጎ ማሳየቱን ወደድኩት። ሰው ሁሉ እንዲያነበው ፈለግሁ። ስለዚህ ልተረጉመው ወሰንኩ። የደራሲውን አድራሻ ከጉግል ላይ አፈላልጌ ፍቃዱን ጠየቅኩት። የተቀረው፣ … እንደሆነው ነው።
በሌላ በኩል “Mine to Win” ደግሞ፣ ሕይወት ተፈራ ለማስተርጎም ፈልጋ ወዳጅ ጓደኞቿን ተርጓሚ እንዲጠቁሟት ስትጠይቅ፣ የኔ ስም በሁለት ወገን ይደርሳታል። “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ”ን ትርጉም ብዙ ሰው ወዶት ስለነበር ነው እኔን መጠቆማቸው። ነገር ግን ሕይወት ሶስት ሰዎችን ለማወዳደር ነበር የፈለገችው። በተለይም ደግሞ “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ”ን አላነበበችውም ነበርና፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በስልክ ስንነጋገር፣ ይህንኑ ገልጻ ከ“Mine to Win” አንድ ምእራፍ ብቻ ሰጥታኝ፣ ከሌሎች ሁለት ሰዎች ጋር እንደምታወዳድረኝ ነገረችኝ። ተወዳደርኩ። ዳኞች እኛ ተወዳዳሪዎች ያላውቅናቸው ሰዎች ናቸው፤ እራሷም አልዳኘችም።
ከጥቂት ጊዜ በኋላ፣ የመጽሐፉ ታሪክ የሚያጠነጥንበትን መቼትና  ሁኔታ የሚመጥን ረቂቅ በማቅረቤ እኔ እንዳለፍኩ ተነገረኝና ስራውን ጀመርኩ። በእርግጥ ሙሉ የትርጉም ስራውን ከመጀመሬ በፊት የእንግሊዝኛውን መጽሐፍ ሳነበው ከዋናው ገጸ ባሕሪይ ከተውኔ (ተዋነይ) ጋር ልባዊ ቁርኝት መፍጠር ያስቻሉኝን በርካታ ነገሮች አገኘሁና፣ ተወዳድሬ እንዳገኘሁት ስራ ሳይሆን ፈልጌ፣ ጠይቄ  የተረጎምኩት ያህል አቅሜ የቻለውን ሁሉ ለማድረግ በቂ ውስጣዊ ግፊት ነበረኝ።
ከእነዚህ ሥራዎች በፊት የትርጉም ልምድ ነበረሽ?
ከዚህ በፊት የነበረኝ የትርጉም ልምድ በአብዛኛው ግጥሞችን መተርጎም ነበረ። ሙሉ ስራ ሳይሆን፣ እንዲሁ እዚህም እዚያም ሳነባቸው የወደድኳቸውንና  ስሜቴን የነኩትን አንዳንድ ግጥሞች ተርጉሜያለሁ። “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ”ን ተርጉሜ ስጨርስ ጉዳዩ ለራሴውም ጥያቄ ሆነብኝ። አንብቤው እዚያው ለመተርጎም የወሰንኩበትን ቁርጠኝነት ከየት አመጣሁት? እስካሁን ለምን ሙሉ ስራ ለመስራት አልተነሳሁም ነበር? እና የመሳሰሉት ጥያቄዎች ውስጤ ይመላለሱ ነበር። ይህን ጊዜ ነው ለመጀመሪያ  ጊዜ ትርጉም የሞከርኩበት አጋጣሚ ታልሞ  እንደተረሳ  ህልም ትውስ ያለኝ። አምስተኛ  ክፍል ነበር። I am Legend የተባለውን የሪቻርድ ማቴሰን መጽሐፍ ቤት ውስጥ አግኝቼ አንብቤዋለሁ፤ እንግዲህ በአምስተኛ ክፍል እንግሊዘኛ ምን ያህል ገብቶኝ እንደሆነ አሁን በዝርዝር መግለጽ አልችልም። የማስታውሰው ግን አንዲት ጓደኛዬን “እንተርጉመው” ብያት በጠራራ ፀሐይ ይዘነው ሜዳ ላይ ቁጭ ብለን እንደሞከርን ነው። እንደሚጠበቀው አንድ አረፍተ ነገር እንኳን አልተሳካልንም።
ሥነጽሑፍን በተመለከተ፣ ግጥም እጽፍ ነበር፤ አብዛኛዎቹ በዩኒቨርሲቲ ቆይታዬ የተጻፉና ባህል ማእከል የቀረቡ ናቸው። ገጣሚ እንዳልሆንኩ የገባኝ ለታ ግን መጻፍ ተውኩ። ባለፈው አስራ ሁለት አመት ውስጥ፣ እጅግ በጣም ስሜቴን የነኩት ነገሮች ገጥመውኝ፣ አንድ ሶስት ግጥም ሳልጽፍ አልቀረሁም። ፌስቡክ ላይ ተለጥፈዋል። ድሮ የሞካከርኳቸው አጫጭር ልቦለዶችም ነበሩኝ።
ብዙ ጊዜ የምትጠቀሚው የትርጉም ስልት ምን ዓይነት  ነው?
ስለ ትርጉም ስልቴ ለማብራራት “ኀሠሣ” ላይ የአርትኦት ስራ የሰራው ይኩኖአምላክ መዝገቡ በአንድ ወቅት ያለኝን ላካፍል። ስለ “ኀሠሣ” አንዳንድ ነገር ለመነጋገር እኔና  ሕይወት ተፈራ አግኝተነው ነው። “የሶሻሊስቱ ጠንቋይ ጉዳይ”ን ቀድሞ አንብቦት ነበረና ስለ ትርጉም ስልቴ የሚያስበውን እንደሚከተለው አጫወተኝ። ወደ እኛ ከመምጣቱ በፊት የሚነበብ ነገር ሲያገላብጥ፣ አንድ ሰው ስለ ተርጓሚዎች በጣልያንኛ የተናገረውን ነገር አግኝቷል። ሰውየው “Traduttore traditore” ነው መሰለኝ ያለው። Translator, traitor ለማለት ነው በእንግሊዘኛ፤ “ተርጓሚ ከሃዲ ነው” እንደማለት።
ማለትም አንድ ሰው የትርጉም ስራ ሲሰራ የሚከናወን የፈጠራ ስራ አለ፣ ምንም ያህል እናት/ምንጭ ስራውን ተቀራርቦ ሊተረጉም ቢሞክር እንኳን፣ የቋንቋ ብቃት፣ የራሱ አመለካከትና ንቃተ ህሊና፣ የራሱ ባህልና ስነልቦና የመሳሰሉት ነገሮችን ይጨምርበታል። ስለዚህ ትርጉሙ ዋናውን ሊመስል አይችልም። ተርጓሚው የራሱን አረዳድ ነው የሚጽፈው፤ በመሆኑም ከሃዲ ነው። ዋናው ባለስራ ወይም ዋናው ስራ ላይ የሚፈጽመው ክህደት አለ የሚል ነገር አጫወተኝና፣ “አንቺ ግን ከሃዲ አይደለሽም” አለኝ በስተመጨረሻ። ትክክል ነው፤ እናት ጽሑፉ የግድ መጨመርን ወይም መቀነስን ካልጠየቀ በስተቀር (ለሚተረጎምበት ቋንቋ አንባቢዎችን ስምም ለማድረግ ሲባል) እንደተጻፈው መተርጎምን እመርጣለሁ። ይህንን ስልት አስቤበት መርጬው አይደለም። እስከዛሬ  ትርጉም ስሞክር ልቦናዬ  የመራኝ በዚያ  መንገድ ስለነበረ፣ መጠቀም የቀጠልኩበት ስልት ነው።
ዕለታዊ አሰራሬ ጠዋት ራሴን ከማስደሰት ይጀምራል። ቁርስ፣ ቡና በትልቅ ኩባያ፣ ትንሽ ፌስቡክ። ከዚያ ስራ፣ ምሳ፣ ለኻያ ደቂቃ ማሸለብ፣ ተነስቶ ስራ መቀጠል፣ ከምሽቱ አንድ ሰዓት ላይ ስራ አቁሞ ሌሎች የሚያስደስቱኝን ነገሮች ማድረግ። በሌሎች የስራ ወይም የማህበራዊ ኑሮ ጉዳዮች ያልተረበሸ የስራ ቀኔ ይህን ይመስላል። በእርግጥ በየመሃሉ ቤቴ ውስጥ በተሰናዱት የዘቢብ፣ የቴምር፣ የሱፍ ፍሬ፣ የኦቾሎኒና የመሳሰሉት ጣቢያዎች ቆም እያልኩ ነዳጅ እሞላለሁ!
“ኀሠሣ”ን ስትተረጉሚ ከእናት ድርሰቱ (Mine to Win) ወጣ ለማለት አልሞከርሽም ?
ከላይ እንዳልኩት ‘traditore’ ላለመሆን የተቻለኝን ያህል ሞክሬያለሁ። እናት ድርሰቱ የተጻፈበት ዘመን መንፈስ (Zeitgest)፣ የተገለጸው የአኗኗር ሁኔታ፣ የአነጋገር ዘዬ፣ የአመለካከት አጥናፍ እንዳለ ወደ አማርኛ ቢመለስ፣ ትርጉሙ የመጣፈጥ እድሉ ይጨምራል። ደግሞ ይዘቱ ውስጥ የሚገኘው ቅኔ ነው፣ ትምህርት ነው፣ ኢትዮጵያዊ ጥበብና ፍልስፍና ነው፤ ሕግጋትና ማፈንገጦች ናቸው። ለምን ወጣ ብዬ ለመሄድ እሞክራለሁ? ለዛውን ማሳጣት ይሆናል።
የዘመኑን (19ኛ ክ/ዘመን) የንግግር ዘዬ ለማምጣት እንዴት ተሳካልሽ ?
ያደረግኩት ዝግጅት የተጠቀምኩትን ስልት ይገልጻል ብዬ አስባለሁ። በመጀመሪያ የሥነጽሁፍና የታሪክ ምሁር በሆነ ውድ ጓደኛዬ ትጋት፣ ለዚህ ስራ ዝግጅት ላነባቸው የሚገባኝ መጻሕፍት ዝርዝር ወጣ። እኔም የራሴን አከልኩበት። ከዚህ በኋላ ዝርዝሩ ላይ ያሉትን መጻሕፍት አሰባሰብኩ። መጻሕፍቱ በአብዛኛው በ19ኛው ክ/ዘመን ጀምሮ እስካሁን ድረስ የነበሩ/ያሉ ሊቃውንት፣ መምህራን፣ ዲያቆናት፣ ጸሐፌ ዜና መዋዕሎች፣ ደራሲዎች የጻፏቸው፣ ወይም ስለእነሱ የተጻፉ ናቸው። አንዳንዶቹ እኔ ራሴ ቤት ውስጥ ነበሩኝ፣ ሌሎች በግዢ፣ በውሰት ወይም ከበይነ መረብ በማውረድ (ለምሳሌ: የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክ መጻሕፍት) የተገኙ ናቸው።
ቀን ቀን መሰረታዊ የትርጉም ስራውን እየሰራሁ፣ ማታ ማታ እነዚህን መጻሕፍት ማንበብ ጀመርኩ። እያነበብኩም ሊጠቅሙኝ የሚችሉ ቃላትን በማስታወሻ  እየሰበሰብኩ፣ የራሴን ትንሽዬ ሙዳየ ቃላት አዘጋጀሁ። በእርግጥ ከዚህ በፊት የቤተሰብ አባላት ሲነጋገሩ በምሰማበት ወቅት፣ በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ወቅት፣ በንባብ ወቅት፣ ካገኘኋቸው ቃላት በትውስታዬ የተገኙትን ሁሉ በረቂቁ ውስጥ ተጠቅሜባቸዋለሁ። በመቀጠል ረቂቁን የማበልጸግ የመጀመሪያ ዙር ስራ ስሰራ ያጠራቀምኳቸውን ቃላት እንደ ሁኔታው ቦታ ቦታ አገኘሁላቸው። ከገጠር የኑሮ ዘይቤና ከቤተ ክርስቲያን ስርዓት ጋር የተያያዙ ብዙ ቃላትን እናቴ ጠቁማኛለች። በአቅራቢያችን ከሚገኘው ሰዓሊተ ምህረት ቤ/ክ የነበሩ ካህን አገናኝታኝ በቃለ መጠይቅ ብዙ መረጃ ሰጥተውኛል። በዚህ ጊዜ በብዛት ያገኘኋቸው መጻሕፍት የተጻፉት በሸዋ ልሂቃን እንደመሆኑ የረቂቁ አማርኛ የሸዋ አማርኛ ያመዘነበት ይመስለኛል። ጥንታዊዎቹን መዛግብተ ቃላትና ተጨማሪ መጻሕፍትን በመጠቀም በበኩሌ የተቻለኝን ያህል የጎጃምን ዘዬ ለማምጣት ከሰራሁ በኋላ የቀረውን አርታኢዎች እንዲያዩት ተውኩላቸው። ያጎደልኩትን ሞሉልኝ፣ ያጣመምኩትን አቀኑልኝ።
ገና የእንግሊዘኛውን መጽሐፍ ማንበብ ስጀምርና ታሪኩ በ19ኛው ክ/ዘመን አጋማሽ አካባቢ እንደሚያጠነጥን ስረዳ፣ የተገለጸልኝ ነገር የሚተረጎምበት አማርኛ የገጠር አማርኛ ብቻ ሳይሆን፣ የድሮ የገጠር አማርኛ መሆን እንዳለበትም ጭምር ነው። በዘመን ሂደት ቃላትም ጡረታ ይወጣሉና የተገኘው የገጠር አማርኛ ብቻ በቂ ላይሆን ይችላል፤ የቆየ መሆን አለበት፣ አሁን እምብዛም የማንሰማው፣የማንናገረው። ስለዚህ ‘ወደፊት’ ሳይሆን ‘ግፋኝ’ ጊዜውን የበለጠ ያሳያል …  ቅድመ አያቴም፣ አያቴም ለምሳሌ “ተነስተሽ የማትሄጅ?” ሲሉ ሰምቼ አላውቅም። “ተነስተሽ እማትሄጅ?” ግን ይሉ ነበር። አርታኢዎችም በዚህ መንገድ የመጻፉን ሃሳብ አቅርበው ተቀብዬዋለሁ።
መጽሐፉ ውስጥ የምናገኛቸው እንደ ዐወቀ፣ አባ እና  ሠረገላ  ብርሃን ያሉ ሌሎች አውራ ገጸባሕሪያት ደግሞ፣ እንደው ሁሉም አንዳይነትና ልሙጥ እንዳይሆኑ ትንሽ የአነጋገር ልዩነት ቀለም ልቀባባቸው ሞክሬያለሁ። መቼም መቶ በመቶ ተሳክቷል ብዬ አፌን ሞልቼ ባልናገርም፣ አማርኛ እንዳሁኑ ሳይሆን፣ ከሞላ ጎደል በግዕዝ ፊደላት በሚጻፍበት ጊዜ ቃላቱ የሚጻፉበትን መንገድ ለመከተል ስለመረጥኩ ነው፤ ትርጉሙ ጊዜውን እንዲመስል። እንዳልኩት ታሪኩ የሚተረክልን በአንደኛ መደብ፣ በዋናው ገጸባሕሪ በተዋነይ ነው፤ ተዋነይ ደግሞ ሐዲስን ጠንቅቆ፣ ጸሐፌ ዜና መዋዕል ለመሆን የታጨ ሊቅ ነው። አማርኛውን ዛሬ እኛ እንደምንጽፈው እያቀላቀለ ወይም የግዕዝን ድምጾች ባስወገደ መንገድ ይጽፈዋል ተብሎ መቼም አይጠበቅም ብዬ በማሰብ ነው።
የቻልኩትንም ያህል ዋና ዋናዎቹን መዛግብተ ቃላት በመመልከት ለቅሜ ለመጠቀም ጥረት አድርጌያለሁ። ከላይ እንዳልኩት ለጊዜውና ለቦታው እውነተኛ (authentic) በሆኑ ቃላት ነገሮችን ለመግለጽ መሞከሬ እንዳለ ሆኖ፣ አንዳንድ ቃላት በጣም ዘመናዊ (modern) ወይም ዘመነኛ (contemporary) ሲመስሉኝ ቆየት ያለውን አቻቸውን ለመፈለግ ሞክሬያለሁ። አንዳንዴ አሁን ባለንበት ጊዜ እስኪሰለቹ ድረስ የምንጠቀማቸውን ቃላት በደራሲዋ ሕይወት ምክር የቀየርኳቸው ይኖራሉ፤ ለምሳሌ፡- ታዳሚው፣ ታዳሚያንን የሚለውን ትተን፣ ‘እድምተኛው’ን መጠቀም መረጥን።
ከሕይወት ተፈራ ጋር እንዴት ነበር የምትሰሩት?
ትርጉሙን ጨርሼ ነው የሰጠኋት። ያው የመጀመሪያው ምእራፍ የተወዳደርኩበት ነው። ሌሎቹን ጨርሼ፣ በተደጋጋሚ አንብቤና አርሜ ሙሉውን ነው የሰጠኋት። የስራው ሂደት እጅግ አስደሳች ነበር። ሕይወት ተፈራ በጣም አስተዋይ ናት፤ የረሳሁት መስመር ወይም በተሳሳተ መልኩ ተረድቼው የተረጎምኩት መስመር አያመልጣትም፤ የራሷን መጽሐፍ በልቧ ታውቀዋለች። በመሆኑም ረቂቁን አንድ ሶስቴ ኦዲት አድርጌዋለው፤ የጠፉ አናቅጽና  መስመሮች እንዳሉ ቆጠራ።
ያልመሰላት ጉዳይ ላይ በግልጽ ታዋየኛለች፣ ታደምጠኛለች። ወይ አሳምናታለሁ፣ ወይ ታሳምነኛለች። የመጨረሻ ውሳኔ የእሷ ቢሆንም፣ ብዙ ጉዳዮች ላይ እስከ መጨረሻ  ድረስ እንከራከር ነበር። ስለዚህ ራሴን ለመግለጽና ለማስረዳት ምንም ገደብ አላበጀችብኝም። አንዳንዴ እንዴት አድርጌ ሳዋራት እንደነበር ቤት ገብቼ  ሳስበው፣ እንደ እኩያዋ እንዳዋራት ያስቻለኝን ድባብ እንደምን እንደፈጠረችው ይደንቀኛል። የትርጉሙን የመጀመሪያውን ረቂቅ አንብባ በመደሰቷ የራሷን መጽሐፍ “ለካ እንዲህ ቆንጆ መጽሐፍ ነበርን’ዴ?” ያለችኝ ዕለት፣ እኔም እጅግ ደስ ተሰኝቼበታለሁ።
መጽሐፉን አሁን መለስ ብለሽ ስታይው፣ ትርጉምሽ ላይ ማስተካከል የምትፈልጊው ይኖር  ይሆን?
አንዳንድ አሁንም መስተካከል የሚችሉ ነገሮች አይጠፉም። ያው ለረጅም ጊዜ ከእጅህ ሳታወጣ ልታስተካክለው፣ ልታሰማምረው የምትችል ይመስልሃል። ግን የሆነ ቦታ ይህ ሂደት መቋረጥ አለበትና ነው እርማት ማድረግን የምታቆመው። በመሆኑም ትርጉሙን ያነበቡ እንዲሁም የገመገሙ ሰዎች አስተያየታቸውን ሲሰጡ፣ ባለማወቅ፣ በእንዝህላልነት ወይም በተሳሳተ ምክር ምክንያት የተፈጠሩ መስተካከል የሚችሉ ነገሮች ታይተውኛል። ከነዚህ ውጪ ምንም ማከልም ሆነ  ማንሳት አልፈልግም።
በሁለተኛው እትም ላይ ያስተካከልነው የተወሰኑ የፊደል ግድፈቶችን፣ እና አንድን ቃል በተለያዩ ሆሄዎች በመጻፍ የተሰሩ ስህተቶችን ነው። በተጨማሪ፣ ኀሠሣ ላይ የእንግሊዘኛው ርእስ (Mine to Win) ሳይካተት ነበርና የታተመው፣ እንግሊዘኛው መውጣቱን ያላወቁ ሰዎች የየትኛው መጽሐፏ ትርጉም እንደሆነ ጥያቄ ስላበዙ፣ ይህንንም አንድ ላይ አርመናል። እንዲህ አይነት ትናንሽ እርማቶች ናቸው እንጂ ይዘቱ ላይ የተደረገ ለውጥ የለም።
ከትርጉም ሥራዎች ውጭ  የራስሽ ወጥ ድርሰቶች የሉሽም ?
በአሁኑ ሰዓት አቋርጬው የነበረ አንድ ረቂቅ የረጅም ልብወለድ ስራ እጄ ላይ አለ። በቅርቡ እመለስበትና እጨርሰዋለሁ ብዬ አስባለሁ። ያለፈው አርባ አመት የፖለቲካ ታሪካችን በሁለት ትውልድ ደጋግሞ የሚበጠብጠው ቤተሰብ ታሪክ ነው ባጭሩ።
የትርጉም ሥራና ድርሰት ምንና ምን ናቸው ?
ከአሰራር ልማድ (routine) አንጻር ልዩነት የለውም። ከክህሎት አንጻር ግን አሁን ጀማሪ ተርጓሚ አይደለሁም፤ ግን ጀማሪ ደራሲ ነኝ፤ ሙልጭ ያልኩ አማተር። ስልቴን ገና እያፈላለግኩት ነው። ኀሠሣ ስልት ላይ ነኝ ማለት ይቻላል።
የሚቀጥለው ሥራሽ ምን ላይ የሚያተኩር ነው?
ወጥ ስራን በተመለከተ፣ ከላይ በአጭሩ አስቀምጬዋለሁ። ትርጉምን በተመለከተ፣ በአሁኑ ሰዓት በቅርብ ጊዜ ገበያ ላይ ውሎ ተወዳጅነት ያተረፈውን የዮርዳኖስ አልማዝ ሰይፉን “መንገደኛ” ወደ እንግሊዘኛ እየመለስኩ እገኛለሁ። ሌሎችም ልተረጉማቸው የምፈልጋቸው  መጻሕፍት አይጠፉም።




የሚከተለው ተረት “ከብላቴን ጌታ ማሕተመ ሥላሴ ወ/መስቀል ስብስብ ሥራዎች” ያገኘነው ነው፡፡
“ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ ሰው አንዲት ቤት ሊሠራ ፈቀደ፡፡ ነገር ግን ይህ ሰው ተመልካችና ጠንቃቃ አልነበረምና ይህች አዲስ ቤት የምትሠራበትን ጠንካራውን መሬት መምረጡን ትቶ፤ ሥራው የሚፋጠንበትን አኳኋን ብቻ ተመልክቶ፣ ዐቀበት ከሌለው ከረባዳ መሬት፣ እንጨቱንም፣ ደንጊያውንም ያለ ብዙ ድካም ለማግኘት እንዲችል፣ የሚፈቅድለትን ቦታ መረጠ፡፡
ደግሞ የገንዘብ ቁጠባ ያደረገ መሰለውና የቤቱን መሠረት አጎድጉዶ፣ ዝቅ ብሎ ከጥብቅ መሬት ወይም ከደንጊያ ላይ እንደ መሥራት መሠረቱን ሳይቆፍር፣ እንዲያው ካሸዋው ላይ ሰራ ጀመረ፡፡
አንደኛው ሰው ግን በጣም ተመልካችና ጠንቃቃ ነበርና ቤቱን ለመሥራት ባሰበ ጊዜ አወቀድሞ በመልካም አድርጎ፣ አዳጋ ከሆነ ሥፍራ ላይ በጣም ጥንካሬና ጭንጫነት ያለውን መሬት መረጠ፡፡
ይህ ሰው የቤቱን መጠነ ነገር እንጂ ከዚህ ካቀበት ቤት ለመሥራት በድንጋይ፣ በኖራ፣ ባሸዋ በእንጨት ማቅረብ ያለውን ሁሉ ድካምና የገንዘብ ወጪ አልተሰቀቀም፡፡
የመሠረቱም ድንጋይ በሚጣልበት ጊዜ አስቀድሞ የሚበቃ ያህል መጎድጎዱን፤ ከሥርም መሰረቱ የሚያርፍበት ጠንካራ ጭንጫ መሬት መውጣቱን መረመረ፡፡
የብልሁም፣ የሞኙም ሰው ቤቶች ተሠርተው ባለቁ ጊዜ፤ ወዲያው ኃይለኛ ነፋስ ተነሣ፡፡ ግራ ቀኝም ነፈሰ፡፡ ብርቱ ዝናብም ዘነመ፡፡
ፈረፈሮችም፤ ፈፋዎችም፣ ወንዞችም ሁሉ ሞሉ፡፡ ኃይለኛውም ጎርፍ ወደ ዘባጣው ቦታ ካሸዋ ላይ ወደተመሠረተው ቤት በብዛት ይወርድ ጀመር፡፡ ከጥቂት ጊዜም በኋላ ይህ ኃይለኛ ርኅራኄ የለሽ ጎርፍ የቤቱ መሰረት ያረፈበትን አሸዋውን ጠርጎ፤ ወሰደው፡፡ ቤቱም መሰረት ስላጣ እየተነሰነጠቀና እየተገመሰ በየማዕዘኑ ወደቀ፡፡ የቤቱንም ድንጋዮች፣ ወጋግራዎቹንና ካንቾቹን ሁሉ እያንከባለለ እያዳፋ አወረዳቸው፡፡
ከድንይ ላይ የተመሠረተው የሌላው ሰው ቤት ግን እንደዚህ አልሆነም፡፡ ኃይለኛ ነፋስ ነፈሰ። ብርቱ ዝናምም ዘነመ፡፡ ወንዞችም፤ ፈረፈሮችም፤ ፊፋዎችም፣ ሁሉ ሞሉ፡፡ ድንጋዮን የሚፈነቅሉ የሚያንከባልሉ፣ ዛፎችንም ከሥራቸው የሚነቅሉ እጅግ ብርቱ የሆነ ጎርፎች ጎረፉ፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ከቶ ይህ ቤት አልተናወፀም፡፡ ቁጣውንም ሁሉ ምንም ነገር ሳይገኘው አሳልፎታል፡፡
* * *
የሀገራችን ፓርቲዎች በአብዛኛው በአሸዋ ላይ የተሠራው ቤት ዓይነት ናቸው፡፡ ገዥው ፓርቲ ወይ ኃይለኛው ነፋስ ነው፣ ወይም ደግሞ አለት ላይ የተሠራው ቤት ነው፡፡ ጠንካራው ቤት ላይ ግትርነት ተጨምሮ ሲታሰብ፣ ክፉውን ጊዜ መቋቋም ብቻ ሳይሆን ክፉ መሆንም ይመጣል፡፡
ማን አለብኝ ይመጣል፡፡ ይሄ ቢሮክራሲን ሲንተራስ ደግሞ ይብስ የቤት- ጣጣ ይኖረዋል! ከዚህ ያውጣን! የፖለቲካ ፀሀፍት የኋላ-ቀር አገራት ፓርቲዎች ጣጣ የሚጀምረው ከ bureaucratization of the party ነው ይላሉ፡፡ ይህም፤ ጥንትም ሆነ አሁን፤ በሀገራችን አንዱ የገዢ ፓርቲ ዋና ችግር ሲሆን በቢሮክራሲው ውስጥ ጉዳይ ፈፃሚና አስፈፃሚ አባላትን መሰግሰግ ነው፡፡ ቢሮክራሲያዊ ፓርቲ መፍጠር ነው!
ገዥው ፓርቲ ራሱ ፖሊሲ ይቀርፃል፡፡ ራሱ ይተገብራል፡፡ ይህን የሚፈፀመው መንግሥት ውስጥ ባሉ አባላቱ አማካኝነት ነው፡፡ ስለሆነም ቢሮአዊ ፓርቲ ይሆናል ማለት ነው! የቻይና ኮሙኒስት ፓርቲ፤
መንግሥት መዋቅር ውስጥ ባሉ አባላቱ የፓርቲውን ዓላማ የሚፃረር አቋም ያላቸውን ሰዎች የፖለቲካ እንቅስቃሴ ይገድባል፡፡ በተግባር ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ እንዳይፈጠር ማድረጉ ነው! ወይ በከፊል ለመንግሥት የገበረ ፓርቲ አሊያም ፀባይ ያለው ተቃዋሚ/ ተንበርካኪ ፓርቲ እንዲፈጠር ያደርጋሉ- Mute opposition እንዲሉ፡፡ የፓርቲ አባላት እጅግ ኃይለኛ/ ጠንካራ የሚባሉትን የመንግስት ቢሮዎች እንዲይዙ ይደረጋል/ተደርጓል፡፡
ከዚያም ሁኔታዎችን ይቆጣጠራሉ፤ አባላት ይመለምላሉ፡፡ የማይመቿቸውን ሰዎች ከቢሮ ያርራሉ፣ የሚሆኑዋቸውን ሰዎች በወገናዊ መንገድ ያስቀጥራሉ! መተካካት ይሉታል ሲፈልጉ፡፡ የራሳቸውንም ሰው የሚያባርሩበት ጊዜ አለ፡፡ አንደሌኒን “The Party purges itself” ይላሉ፡፡ ፓርቲ ራሱን አጠራ፤ እንደማለት ነው! ቢሮክራሲና ፓርቲ ከተጋቡ ቆይተዋል፡፡
ቢሮክራሲና ፓርቲ ካልተለያዩ ሁሌ መዘዝ አለ-ወገናዊነት፣ ዘመዳዊነት፣ ብቃት-አናሳነት፣ አድር-ባይነት፣ ግትርነት፣ ኢፍትሐዊነት ወዘተ ዝርያዎቹ ናቸው፡፡ ስልቹነትና ምን-ግዴነት ዋና ጠባይ ይሆናል። የመንግሥት መመሪያን ከፓርቲ መምሪያ መለየት አደጋች ይሆናል፡፡
የሥራ ትጋትና ፍጥነት አይኖርም!
አንድ ጊዜ ፕሬዚዳንት ጂሚ ካርተር ግብፅን ሲጎበኙ፤ “ታላቁን ፒራሚድ ለመገንባት ሃያ አመት ነው የፈጀው” ተባሉ፡፡ ይሄኔ ካርተር፤
“የመንግሥት ድርጅት እንዲህ በፈጣን ጊዜ መገንባቱ አስደንቆኛል” አሉ፡፡ አግቦኛ ንግግር ነው፡፡ ቢሮክራሲ ሥራ አፋጥኖ አያውቅማ! የቢሮክረሲ ቀይ-ጥብጣብ (bureaucratic red-tape) ሁሌም የሥራ፣ ብሎም የዕድገት አንቅፋት ነው፡፡ በተለይ ፓርቲው ድልን የተቀዳጀው የቀድሞን ሥርዓት በኃይል አሰገድዶ ገርስሶ ሲሆን፤ እንደ ብዙ የአፍሪካ መንግሥታት ሁሉ፤ ዘርፈ-ብዙ የአገዛዝ ውጥንቅጥ ውስጥ ይዘፈቃል፡፡ ሁሉን ነገር በገዢ ፓርቲ ኮሚቴ እንምራ የሚል ዘይቤ ይጫነዋል፡፡
እኔ ሁልጊዜ የማስበው “ግመል፤ በኮሚቴ ፈረስ ናት ተብላ የተሰራች፣ እንስሳ ናት!” ብዬ ነው - ብሏል ፍሬዲ ሌከር የተባለ የፖለቲካ ተንታኝ፡፡
በየመስሪያ ቤቱ ስብሰባዎች ወሳኝ ሚና አላቸው፡፡ ግምገማዎች፣የቅጥርና የማባረር ሥርዓቶች፣ የቀረጥ አያያዦች፣ የሙስና አፈራረጆች ላይ ሁሉ የስብሰባ ሂደቶች፣ የኮሚቴና የቡድናዊነት (groupism) ስሜትን የተላበሱ መሆናቸው፣ አንዱ የፓርቲ ቢሮክራሲያዊነት ባህሪ ነው፡፡
አንድ ያልታወቀ ፀሀፊ፤
“አንድን ሀሳብ መግደል ከፈለክ ወደ ስብሰባ ውሰደው” ይላል፡፡ በእርግጥም በስብሰባ ሀሳብን ማሳደግም፣ መግደልም ይቻላል፡፡ ዋናው ጉዳይ የፓርቲ መዋቅር በቢሮክራሲ ውስጥ፤ ሥር- እንዲሰድ የማድረግ ነገር ነው፡፡ ያለፈው መንግሥት፤ ፍጥጥ ያለና ዓላማው ፖለቲካዊ ተልዕኮን ያነገበ “የለውጥ ሃዋሪያ” የሚባል ወኪል ነበረው!!
የመንግሥት ሶሻሊዝም፣ አንድ ነጠላ፣ የተማከለ፣ ፈላጭ-ቆራጭ አምባገነን ፈጥሮ፣ ፍፁም የሆነ ሥልጣንን ይይዛል፡፡ ይሄንን የሚፈፅመውም ባሉት ቢሮክራሲያዊ ወኪሎች ነው፤ ካፒታሊዝም ደግሞ ብዙ ትናንሽ አምባገነኖችን መፈልፈል ነው ሥራው፡፡ እያንዳንዱ አምባገነን የየራሱን የንግድ ግዛት ይመራል! (አልደስ ህክስ ሌይ ነው ያለው) በፖለቲካዊ መልኩ ፈላጭ-ቆራጭ፣ በኢኮኖሚ መልኩ ደግሞ በዝባዥ /ሙሰኛ) ኪራይ ሰብሳቢ ነው፡፡ ችግሩ አፍጦ የሚመጣው እንደ ዛሬው ፖለቲከኛውን ከሙሰኛው ነጥሎ ማየት ሲያቅት ነው! ይሄ ሀገራችንን በጣም በረዥሙና በሰፊ መረብ የሚፈታተን፣ ከተልባ ውስጥ አፈር የማበጠር ያህል አስቸጋሪ አባዜ ነው!!
ይሄን አባዜ በቀላሉ መገላገል አይቻልም፡፡ ምነው ቢሉ በአብዛኛው፤ በቅጡ ስንመረምረው ከፊውዳሊዝም የወረስነው ምቀኝነት፣ ተንኮልና ደባ በውስጡ የተንሰራፋ ስለሆነ ነው! የእኔ ፓርቲ ቅዱስ፣ የአንተ ፓርቲ እርኩስ ማለት ሳያንስ፤ ያንተ ፓርቲ ካልወደቀ የኔ ፓርቲ አይለመልምም ወደሚል እሳቤ መጓዝ ይመጣል፡፡ ስለዚህ “ያንተ ፓርቲ ይውደም!” ይሆናል መፈክሩ፡፡ ዛሬ በይፋ የምናየው “ሞኝ ነጋዴ በራሱ መቀማት ሳያዝን የጓደኛው ማምለጥ ይቆጨዋል” የሚለው ተረት በንግድም፣ በፖለቲካውም በፓርቲ ውስጠ-ነገር፣ በመከላከያም፣ በልማት ፕሮጄክትም፣ በትምህርትም ውስጥ ይሰራል፡፡ ቆም ብለን አካሄዳችንን እንመርምር!!