Administrator

Administrator

ስንፍና የኃጢያቶች ሁሉ ሥር ነው፡፡
   የግሪካውያን አባባል
እርቃኑን የተወለደ መልበስ ያሳፍረዋል፡፡
   የግሪካውያን አባባል
ወይ በጊዜ አግባ ወይ በጊዜ መንኩስ፡፡
  የግሪካውያን አባባል
በወይን ጠጅ ውስጥ እውነት አለች፡፡
  የሮማውያን አባባል
እናትና ልጅ ሲጣሉ፣ ሞኝ እውነት ይመስለዋል፡፡
  የአፍጋኒስታውያን አባባል
ድመቶች አይጥ የሚይዙት እግዚአብሔርን ለማስደሰት ብለው አይደለም፡፡
  የአፍጋኒስታውያን አባባል
ሞት ሲመጣ ጥሩንባ አይነፋም፡፡
  የኮንጎዎች አባባል
ስለ እሳት ማውራት ድስቱን አያበስለውም፡፡
  የአፍሪካ አሜሪካውያን አባባል
በእናቱ ጀርባ ላይ የተቀመጠ ህፃን የመንገዱን ርዝመት አያውቀውም፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል
ቢራቢሮ መብረር ስለቻለች ብቻ ወፍ ነኝ ብላ ታስባለች፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል
እስስት ቀለሟን እንጂ ቆዳዋን ፈፅሞ አትቀይርም፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል
ቢላ ባለቤቱን አይለይም፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል
የክፋትን ዘር በጊዜ ካላጠፋኸው አንተኑ ያጠፋሃል፡፡
  የቻይናውያን አባባል
ባሏ ከሞተ ሴት ጋር ግንኙነት ከመጀመርህ በፊት፣ ባሏን የገደለው ምን እንደሆነ መጠየቅ አለብህ፡፡
  የአፍሪካውያን አባባል

በወጣቷ የፊልም ባለሙያ ሕይወት አድማሱ የተሰራው “አዲስ ዓይኖች” የተሰኘው አጭር ፊልም በዓለም አቀፎቹ የቬነስና ቶሮንቶ ፊልም ፌስቲቫሎች ላይ እንዲታይ መመረጡ ተገለፀ፡፡
ፊልሙ አንዲት የ13 ዓመት ሴት ልጅ የሚጋጥማትን አካላዊና የስሜት ዕድገት ለውጥ ተከትሎ ከማህበረሰቡ ጋር የምትፈጥረውን ግጭት የሚያሳይ ነው ተብሏል፡፡
የፊልሙ ፀሐፊና ዳይሬክተር ህይወት አድማሱ፤ በመላው ዓለም ካሉ 10 ባለተሰጥኦ ወጣት የፊልም ሰሪዎች አንዷ ሆና በቶሮንቶው የፊልም ፌስቲቫል ለሚካሄድ ልዩ ፕሮግራም በመመረጥ ከአፍሪካ ብቸኛዋ እንደሆነች ገልፃለች፡፡
“አዲስ ዓይኖች” በእንግሊዝና በፈረንሳይ የፊልም ኩባንያዎች ፕሮዱዩስ እንደተደረገ ወጣቷ ተናግራለች፡፡
ህይወት በኤሌክትሪክና ኮምፒዩተር ኢንጂነሪንግ የመጀመሪያ ዲግሪዋን ያገኘች ሲሆን በብሉናይል የፊልምና የቴሌቪዥን አካዳሚ ገብታም የፊልም ጥበብን ተምራለች፡፡ ወጣቷ በተለያዩ ዓለም አቀፍ የፊልም ዎርክሾፕና ስልጠናም ላይ መካፈሏንም ጠቁማለች፡፡

በፈቃዱ ሲሳይ የተፃፈው “ምፅኣተ ዓም-ሓራ… በአዲሶቹ ዓም-ሓሮች” የተሰኘ ፖለቲካዊ ልቦለድ መፅሃፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ በ269 ገፆች የተቀነበበው ልቦለዱ፤ ለአገር ውስጥ በ75 ብር፣ ለውጭ አገር በ25 ዶላር ይሸጣል፡፡

 በሲሳይ መኳንንት የተዘጋጀው “አይፈራም ጋሜው እና ምናባዊ እንግዶቹ ቁ.2” ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ “ይህ… መፅሃፍ ከቅፅ 1 ጋር በይዘት ተመሳሳይነት ስላለው ተከታይ ክፍል ሆኖ የተዘጋጀ ሲሆን የመጀመሪያውን መፅሃፍ አግኝቶ ለማንበብ ያልቻለ አንባቢ ቢኖር ይህን ተከታይ መፅሃፍ ብቻ በተናጠል ሊያነበው ይችላል” ብሏል - ደራሲው መቅድም በሚል ርዕስ ባሰፈረው ማስታወሻ፡፡
የቀድሞውም ሆነ የአሁኑ መፅሃፍ በንግግር ልውውጥ ላይ የተመሰረቱ ሃሳቦችን የሚያስተላልፉ መሆናቸውን የጠቆመው ደራሲው፤ ከአገር ውስጥ ከቀድሞው የአገሪቱ መሪዎች  ከኮሎኔል መንግሥቱ ኃይለማርያምና ከጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ጋር፣ ከውጭ ከኔልሰን ማንዴላ፣ ኦፕራ ዊንፍሬይ፣ ማይክል ጃክሰንና ሌሎች ታዋቂ ሰዎች ጋር ምናባዊ ቃለ ምልልስ ማድረጉን ገልጿል፡፡ መፅሃፉ ለአገር ውስጥ በ75 ብር፣ ለውጭ አገራት በ10 ዶላርና በ8 ዩሮ ለገበያ ቀርቧል፡፡

የደራሲ ኤልያስ ማሞ “እንጦሽ”፣ “ውቤ ከረሜላ -1” እና “ጉጉት” የተሰኙ ሶስት መፃህፍት ነገ ጠዋት በ 4 ሰዓት በብሔራዊ ቤተ መዛግብትና ቤተ መፃህፍት ኤጀንሲ አዳራሽ ይመረቃሉ፡፡
“እንጦሽ” በ2006 ዓ.ም ለንባብ የበቃ የአጫጭር ልቦለዶች ስብስብ ሲሆን “ውቤ ከረሜላ - 1” የተለያዩ ማህበራዊ ጉዳዮችን የሚዳስስ መፅሀፍ ነው፡፡ በነገው እለት ለንባብ የሚበቃው “ጉጉት”፤ የ“ውቤ ከረሜላ” ሁለተኛ ክፍል እንደሆነ ታውቋል፡፡
ሶስቱም መፃህፍት እያንዳንዳቸው ከ230 ገፆች በላይ ያሏቸው ሲሆን “እንጦሽ” በ48 ብር፣ “ውቤ ከረሜላ” በ50 ብር እንዲሁም “ጉጉት” በ60 ብር ለገበያ መቅረባቸው ተገልጿል፡፡

   በዮፍታሄ ብርሃኔ የተፃፉ ግጥሞችን ያካተተው “በከንፈር እምጷታ” የተሰኘ የግጥም መድበል ከትላንት በስቲያ ምሽት በዋቢሸበሌ ሆቴል ተመረቀ፡፡ በ64 ገፆች ከ 460 በላይ አጫጭር ግጥሞችን ያሰባሰበው መድበሉ፤ በ30 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Monday, 31 August 2015 09:39

የኪነት ጥግ

ለእይታ የቀረበው ሥነጥበባችን አይደለም፤ ልባችን ነው፡፡
   ጌሪ ሆላንድ
ሰዎች ስዕሎችን ለመስቀል ለምን ግድግዳን ብቻ እንደሚጠቀሙ ግራ ይገባኛል፡፡
   ፍሪትዝ ፐርልስ
ሳያሰልሱ ሥራን ለዕይታ የማቅረብ ጫና በየቀኑ እንድስል ያነሳሳኛል፡፡
   ሊንዳ ብሎንድሄይም
ስቱዲዮ ፋብሪካ ሳይሆን ቤተ-ሙከራ ነው፡፡ አውደ ርዕይ የሙከራዎችህ ውጤት ነው፤ ነገር ግን ሂደቱ ማብቂያ የለውም፡፡ ስለዚህ አውደ ርዕይ መደምደሚያ አይደለም፡፡
   ክሪስ ኦፊሊ
ታሪክ ጥቂት ኦሪጂናሌና በርካታ ቅጂ ስዕሎችን የያዘ ቤተ-ሥነጥበብ ነው፡፡
   አሌክሲስ ዲ ቶክኪውቪሌ
በእኔ ቤተ-ሥነጥበብ ላይ ፀሃይ ፈፅሞ አትጠልቅም፡፡
   ላሪ ጋጐስያን
ቤተ-ሥነጥበብ ለብዙሃኑ የሥራ ዕድል እየፈጠረ ነው፡፡
   ኪም ዌስቶን
የሙዚየም ዋነኛ ዓላማ፤ ሰዎች የዘመናችንን የእይታ ጥበብ እንዲያጣጥሙ፣ እንዲረዱና እንዲጠቀሙ ማገዝ ነው፡፡
   አልፍሬድ ኤች.ባር ጄአር
የስቱዲዮዬ በር ላይ ያለው ማስጠንቀቂያ፤ “በራሪ ብሩሾችን ተጠንቀቁ” የሚል ነው፡፡
   ኧርል ግሬንቪሌ ኪሊን
ፒፓህን ለማጨስ ስቱዲዮ ግሩም ስፍራ ነው፡፡
   ጆአኩዊን ሶሮላ
በሙዚየም ውስጥ ስትሆን በዝግታ ተራመድ፤ ግን መራመድህን አታቋርጥ፡፡
   ጌርትሩድ ስቴይን
ሁሉም ታላላቅ ስዕሎች የማታ ማታ የሚከትሙት ሙዚየሞች ውስጥ ነው፡፡
   ዣኪውስ ባርቢዩ

 ክፍል 3
በ5ሺ ሜ በሁለቱም ፆታዎችና በሴቶች ማራቶን ተጨማሪ ሜዳልያዎች ይኖራሉ፡፡
ገንዘቤ በ5ሺ ለሁለተኛ የወርቅ ሜዳልያ ተጠብቃለች፤ ሪከርዱን ለመስበር እንደምትችልም ተናግራለች
በታክቲክ መበላሸት፤በቡድን ስራ ማነስና በአጨራረስ ድክመት ውጤት ጎድሎበታል፡፡
ከ1 ዓመት ያነሰ ጊዜ ለቀረው ኦሎምፒክ ከሳምንት በፊት በወንዶች ማራቶን የተጀመረው 15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና  ነገ በሴቶች ማራቶን ፍፃሜውን ያገኛል፡፡ በዓለም  ሻምፒዮናው ኢትዮጵያ ከ2 ዓመት በፊት በሞስኮ ያገኘችውን የ3 ወርቅ፤ ሁለት ብር እና የነሐስ ሜዳልያ ስኬት ለማሻሻል ይቅርና ለመድገም ፈተና ይሆንባታል፡፡ ሻምፒዮናው ዛሬ እና ነገ ሲቀጥል ኢትዮጵያ በ5ሺ ሜትር በሁለቱም ፆታዎች ለተጨማሪ ሜዳልያዎች ተጠብቀዋል፡፡ ዛሬ በወንዶች 5ሺ ሜትር የ18 ዓመቱ ዮሚፍ ቀጀልቻ እና፤ ኢማና መርጋ ከ32 ዓመቱ ሞ ፋራህ ጋር ከባድ ትንቅንቅ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ሞፋራህ በዓለም ሻምፒዮናው በ5ሺ ሜትር ለሶስት ጊዜያት አከታትሎ ለማሸነፍ የበቃ አትሌት መሆን እንደሚፈልግ ተናግሯል፡፡ በሌላ በኩል በነገው እለት በሴቶች ምድብ ማጣርያውን በከፍተኛ ብቃት ለማለፍ የቻሉት ገንዘቤ ዲባባ እና አልማዝ አያና በዋናነት እርስ በራሳቸው በሚያደርጉት ፉክክር የዓለም 5ሺ ሜትር ሪከርድ ሊሰበር እንደሚችል ግምት እየተሰጠ ነው፡፡ በጉዳዩ ላይ አስተያየት የሰጠችው የ1500 ሜትር የወርቅ ሜዳልያ አሸናፊ ገንዘቤ ዲባባ ‹‹ በ1500 ሜትር ማሸነፌ በራስ መተማመኔን ጨምሮታል፡፡ በፍፃሜ ሊገጥም የሚችለውን ማወቅ ባይቻልም፤ በጥሩ ብቃት ከተወዳደርኩ የ5ሺ ሪከርድን ሊሰብር የሚችል ፈጣን ሰዓት የማስመዘግብ ይመስለኛል፡፡›› በማለት ተናግራለች፡፡
ኬንያ እና የሜዳልያ ስብስብ ደረጃ
በቤጂንግ ከተማ በሚገኘው የወፍ ጎጆ ስታድዬም ላለፉት  ሰባት ቀናት ሲካሄድ በቆየው 15ኛው የዓለም አትሌቲስ ሻምፒዮና 207 አገራትን የወከሉ 1933 አትሌቶች በሁለቱም ፆታዎች በ47 የውድድር መደቦች  በመሳተፍ ላይ ናቸው፡፡ 36 አገራት ቢያንስ አንድ ሜዳልያ በማግኘት የደረጃ ሰንጠረዥ ውስጥ ገብተዋል፡፡ በሜዳልያ ስብስብ  ኬንያ 6 የወርቅ፤ 3 የብር እንዲሁም 2 የነሐስ ሜዳልያዎች በማስመዝገብ የደረጃ ሰንጠረዡን በአንደኝነት እየመራች ነው፡፡  አሜሪካ 3 የወርቅ፤4 የብር እና 5 የነሐስ ፤ጃማይካ 3 የወርቅ እና 2 የነሐስ ሜዳልያዎች፤ ታላቋ ብሪታኒያ 3 የወርቅ፤ ፖላንድ 2 የወርቅ፣ 1 የብርና 3 የነሐስ ፤ኩባ 2 የወርቅ ፣ 1 የብር፤ ቻይና 4 የወርቅ ፣ 1 የብርና 4 የነሐስ፤  ጀርመን 1 የወርቅ፣ 2 የብርና 2 የነሐስ፤ ኢትዮጵያ 1 የወርቅ እና ሁለት የብር ፤ እንዲሁም ካናዳ 1 የወርቅ 1 የብር እና 2 የነሐስ ሜዳልያዎች በመሰብሰብ እስከ አምስት ያለውን ደረጃ አከታትለው ይይዛሉ፡፡  ቤጂንግ ላይ ኬንያ በዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ ከፍተኛውን ስኬት እያስመዘገበች ነው፡፡ ሻምፒዮናው ሲጠናቀቅ የሜዳልያ ሰንጠረዡን በመሪነት የመጨረስ እድልም ይኖራታል፡፡ በሻምፒዮናው ለኬንያ  የወርቅ ሜዳልያዎች ያስመዘገቡት  በ800 ሜትር ዴቪድ ሩዲሻ፤ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ በ400 ሜትር መሰናክል ኒኮላስ ቤት፤ በ3ሺ ሜትር መሰናክል ወንዶች እዝኬል ኬምቦሚ፤ በ10ሺ ሜትር ሴቶች ቪቪያን ቼሮይት፤ በ3ሺ ሜትር መሰናክል ሴቶች  ኪያን ጄፕኮሚ እንዲሁም በጦር ውርወራ ጁሌዬስ ዮጎ ናቸው፡፡ ከእነዚህ የኬንያ የወርቅ ሜዳልያ ውጤቶች በ400 ሜትር መሰናክል እና በጦር ውርወራ ያገኘቻቸው በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ነው፡፡ በ3ሺ ሜትር መሰናክል የሚያሳዩት የበላይነት መቀጠሉም የሚያስገርም ይሆናል፡፡ ኬንያ በ1970ዎቹ እና 80ዎቹ በአጭር ርቀት ምርጥ አትሌቶች የነበሯት ሲሆን ማናጀሮች እና አሰልጣኞች ወደ ረጅም ርቀት በማተኮራቸው አት ውጤታማነታቸው ቀንሷል፡፡ በሜዳ ውድድር ግን ኬንያ የሜዳልያ ስኬት ስታገኝ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሆን ለኢትዮጵያም ትልቅ ትምህርት የሚሆን ነው፡፡ ኬንያ ባለፉት ሁለት ዓመታት ከዶፒንግ በተያያዘ 40 አትሌቶች በላይ መከሰሳቸው  በስፖርቱ ያላትን ክብር እያጎደፈው ነበር፡፡ ሰሞኑን ደግሞ ከዓለም ሻምፒዮናው ጋር በተያያዘ 2 አትሌቶች ከዶፒንግ በተያያዘ መከሰሳቸው የኬንያን ሰኬት ያደበዘዘው መስሏል፡፡ 2 አትሌቶች በ400 ሜትር ወንዶች እና በ400 ሜትር መሰናክል የሚሳተፉት ናቸው፡፡
ኢትዮጵያን የከዳችው ማራቶን ልዕልቷ
በማራቶን በዓለም ሻምፒዮና ታሪክ ወጣቱ የማራቶን አሸናፊ ለመሆን የበቃው የ19 ዓመቱ ግርማይ ገብረስላሴ ነው፡፡ የወርቅ ሜዳልያውን የወሰደው ርቀቱን  በ2 ሰዓት ከ12 ደቂቃዎች ከ27 ሰከንዶች በመሸፈን ነው፡፡  ኢትዮጵያዊው የማነ ፀጋዬ የዓመቱን የግሉን ፈጣን ሰዓት በ2 ሰዓት ከ13 ደቂቃዎች ከ07 ሰከንዶች  በሆነ ጊዜ አስመዝግቦ የብር ሜዳልያውን ወስዷል፡፡ የኡጋንዳው ሙኖዮ ሰለሞን በ2 ሰዓት ከ13 ደቂቃዎች ከ29 ሰከንዶች በሆነ ጊዜ የነሐስ ሜዳልያውን ለመጎናፀፍ በቅቷል፡፡  በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪኳ ኢትዮጵያ በሁለቱም ፆታዎች ከ1 በላይ የወርቅ ሜዳልያ አግኝታ አለማወቋ ከቤጂንግ በኋላም ቀጥሏል፡፡ በ15ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የመክፈቻ ውድድር በሆነው ማራቶን ላይ የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች የበላይነት ይታይበት ነበር፡፡ የጣሊያን አትሌቶችም ያሳዩት ፉክክር ሊደነቅ ይገባል፡፡ የኢትዮጵያ አትሌቶች  ግን ባላቸው ልምድ ተጠቅመው ውጤታማ መሆን ሲገባቸው ውድድሩን በመቆጣጠር ማራቶኑን መቆጣጠር አልቻሉም፡፡  በማራቶን አሰልጣኞች በኩል የሚሰሩ ተግባራት ተገምግመው የሆነ መዋቅር ሊፈጠር ይገባዋል፡፡ ግማሾቹ አትሌቶች በራሳቸው፤ ሌሎቹ በባሎቻቸው እንዳንዶቹ በማናጀሮቻቸው የሚሰለጥኑበት ሁኔታ ውጤት እያበላሸ መቀጠል የለበትም፡፡  በሌላ በኩል የዓለም ማራቶን ሪከርድን አከታትለው የሰበሩት ሁለት ኬንያውያን  አትሌቶች ከሜዳልያ ውጭ መሆናቸውም ያልተጠበቀ ሲሆን፤ በሌላ በኩል የኦሎምፒክ ሻምፒዮኑ ስቴፈን ኪፕሮችም ሳይሳካለት ቀርቷል፡፡ ከየማነ ፀጋዬ የብር ሜዳልያ ባሻገር  ኢትዮጵያዊያኑ ሌሊሳ ዴሲሳ 7ኛ እንዲሁም ለሚ ብርሃኑ 15ኛ ደረጃ አግኝተው ውድድሩን የጨረሱት፡፡ የብዙ የኢትዮጵያ አትሌቶች ማናጀር የሆኑት ሆላንዳዊው ጆስ ሄርማንስ ስለ ኤርትራዊው አትሌት ግርማይ ገብረስላሴ በሰጡት አስተያየት በቺካጎ ማራቶን በአሯሯጭነት መሳተፉን በዱባይ ማራቶን ሲሳተፍ አቋርጦ መውጣቱን ገልፀው ሳይጠበቅ ማሸነፉ አስገርሞኛል ብለዋል፡፡ በሞቃት አካባቢ ልምምምድ ሲሰራ መቆየቱን የገለፀው ኢትዮጵያዊው የብር ሜዳልያ ባለቤት የማነ ፀጋዬ በበኩሉ ልምድ እንዳለኝ የሚታወቅ ቢሆንም፤ ውድድሩ አስቸጋሪ ነበር፡፡ ከ35 ኪሎሜትር በኋላ ጨጓራ ህመም ገጠመኝ በዚህ ምክንያት ግርማይ አምልጦኝ በመሄድ ሊያሸንፍ ችሏል ብሎ ተናግሯል፡፡
አጨራረሱ የማያምረው የኢትዮጵያ አትሌቶች  የመሰናክል ሩጫ
በ3ሺ ሜትር መሰናክል ውድድሮች ከኢትዮጵያ አትሌቶች የተሻለ ፉክክር ማሳየት የሆነላቸው ሴቶች ናቸው፡፡  በሁለቱም ፆታዎች በ3ሺ መሰናክል ኬንያውያን ፍፁም የበላይነት ማሳየታቸው አልቀረም፡፡ በወንዶች ምድብ ኬንያዊው ኢዝኬል ኬምቦሚ ለ4ኛ ተከታታይ የዓለም ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳልያ በመውሰድ ሲሳካለት እስከ አረተኛ ደረጃም ተከታትለው ገብተዋል፡፡ ማጣርያውን አልፈው ለፍፃሜ መድረስ የቻሉት ቶሎሳ ኑርጊ እና ሃይለማርያም አማረ በፍፃሜው ሲሳተፉ የተለየ ቴክኔክ እና የቡድን ስራ ስላልነበራቸው በአጨራረስም ደካማ በመሆናቸው ከሜዳልያ ፉክክር ውጭ የሆኑት በቀላሉ ነው፡፡ በፍፃሜው ውድድር አሁንም ለኢትዮጵያ የሜዳልያ እድል አጠያያቂው  ሁኔታ የወንዶቹ አትሌቶች የአጨራረስ ብቃት ደካማ መሆኑ ነው፡፡በ3ሺ መሰናክልም በሴቶች ለፍፃሜ የበቁት  ሶፍያ አሰፋ እና ህይወት አያሌው ያላቸውን የዳበረ ልምድ በመጠቀም የተሻለ ፉክክር ቢያሳዩም አጨራረስ ላይ የተለየ ዝግጅት ስላልነበራቸው ውጤቱ ሳይሆንላቸው ቀርቷል፡፡
ለኢትዮጵያ ዱባ እዳ እየሆነ የመጣው 10ሺ
በ10ሺ ሜትር ወንዶች የሞ ፋራህ የበላይነት በቤጂንግም ቀጥሏል፡፡ በውድድሩ የታየው ፉክክር የምንግዜም ምርጥ እየተባለም ሲሆን የኢትዮጵያውያኑ ከጨዋታ ውጭ መሆን ብዙዎችን እያነጋገረ ነው፡፡ የኬንያ አትሌቶች በውድድሩ ላይ በተጠቀሙት የቡድን ታክቲክ ኢትዮጵያውያንን ከፉክክር ውጭ ማድረግ ቢችሉም  ከሞፋራህ ጋር ከባድ ትንቅንቅ ገጥሟቸው የወርቅ ሜዳልያውን ሊነጥቁት አልቻሉም፡፡ ሞፋራህ በ10ሺ ሜትር ንግስናውን ለመቀጠል የበቃው ርቀቱን በ27 ደቂቃዎችከ01.13 ሰከንዶች ጊዜ በመሸፈን ሲሆን፤ ሁለቱ ኬንያያን ጄዮፍሪ ኪፕሳንግ እና ፖል ታንዊ የብርና የነሐስ ሜዳልያዎች አግኝተዋል፡፡ የአሜሪካው ጋለን ሩፕ ደግሞ ከኢትዮጵያውያን የተሻለ ብቃት አስመዝግቦ ሲጨርስ፤ ድሮ ከፍተኛ የበላይነት በማሳየት የሚታወቁት የኢትዮጵያ አትሌቶች ዙር ማክረራቸው ሲጠበቅ ዙሩ ከሮባቸው ከፉክከሩ ተቆርጠው ለመውጣት ተገደዋል፡፡ ይሄው የኢትዮጵያ አትሌቶች ደካማ ብቃት የረጅም ርቀት የምንግዜም ምርጥ አትሌት የሆነው ቀነኒሳ የታል የሚል ጥያቄም በስፖርቱ ቤተሰብ እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ ባለፉት 20 ዓመታት የኢትዮጵያ  አትሌቶች በወንዶች 10ሺ ሜትር ከ1 እስከ 10 ባለው ደረጃ ይወጡ የነበረ ቢሆንም ቤጂንግ ላይ የተሳተፉት አትሌቶች ባልተጠበቀ ሁኔታ ከዚህ ብቃት መውረዳቸው  አሳሳቢ ሁኔታ ነው፡፡ በከፍተኛ ደረጃ የተጠበቀው ኢማና መርጋ ውድድሩን አቋርጦ ለመውጣት ሲገደድ ሌሎቹ አትሌቶች ከ10ኛ በኋላ በመጨረስ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ታሪክ የወረደ ውጤት ለማስመዝገብ ተገድደዋል፡፡
በሴቶች 10ሺ ሜትርም ብዙ የሚያበረታታ ነገር አልታየም፡፡ የወርቅ ሜዳልያውን የወሰደችው ወልዳ ከተነሳች 1 ዓመት እንኳን ያልሞላት ቪቪያን ቼሮይት ናት፡፡ ኬንያዊቷአትሌት ለሁለተኛ ጊዜ በዓለም ሻምፒዮና ጥሩነሽ በሌለችበት የተለመደውን የወርቅ ሜዳልያ ከኢትዮጵያ በመንጠቅ ማሸነፏም ነው፡፡ የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ለ10ኛ ጊዜ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና የወርቅ ሜዳልያ መውሰዳቸው አንድ የሚያኮራ ሁኔታ ነው፡፡በዚህ ውድድር በርቀቱ ብዙም ልምድ የሌላት ገለቴ ቡርቃ በሩጫ ዘመኗ ከፍተኛ የሚባለውን ውጤት በብር ሜዳልያ ማስመዝገቧም ጥሩ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ይሁንና በመጨረሻዎቹ 100 ሜትሮች ገለቴ ቡርቃ የወርቅ ሜዳልያውን ለመውሰድ ያደረገችው ሙከራ በአጨራረስ ላይ ብዙ ባለመስራቷ የተሳካ አልነበረም፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት የወርቅ ሜዳልያ ያሸነፈችውን ጥሩነሽ ዲባባ ተከትላ በመግባት የብር ሜዳልያ የወሰደችው በላይነሽ ኦልጅራ ከሜዳልያ ውጭ ሆና ስትጨርስ ብዙም ልምድ ያልነበራት አለሚቱ ሃሮዬ ተፎካካሪነት አልነበራትም፡፡ አሜሪካዊት አትሌት በዚህ ውድድር የነሐስ ሜዳልያ ለመውሰድ መብቃቷ ተፎካካካሪነታቸው እያደገ መምጣቱን ያሳየ ነበር፡፡
በ1500 ሜትር የገንዘቤ ወርቅ የተሻለው ውጤት
በ1500 ሜትር ሴቶች ገንዘቤ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያውን በፍፁም የበላይነት ለመውሰድ በቅታለች፡፡ እስከትናንት ኢትየቶጵያ ያስመዘገበችው ትልቁ ስኬትም ነው፡፡ ገንዘቤ የዓለም ሪከርድን ዘንድሮ እንደማስመዝገቧ ውጤቱን የተለየ ባያደርገውም የወርቅ ሜዳልያው በርቀቱ በኢትዮጵያ የዓለም ሻምፒዮና ታሪክ ለኢትዮጵያ የመጀመርያው፤ ለራሷ ገንዘቤ በዓለም ሻምፒዮናው በትራክ የመጀመርያ የወርቅ ሜዳልያ ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ በሴቶች 1500ሜ ለሶስቱ ሜዳልያዎች ጠቅላይነት የኢትዮጵያ 3 አትሌቶች ከመጀመርያው ዙር ማጣርያ በኋላ ተጠብቀው ነበር፡፡ ከገንዘቤ ጋር ለፍፃሜ የደረሰችው ዳዊት ስዩም ሜዳልያ ውስጥ ለመግባት ከባድ ፉክክር የገጠማት ከትውልደ ኢትዮጵያዊቷና ለሆላንድ የምትወዳደረው ሰይፋ ሃሰን ነበር፡፡ በዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ታሪክ ለኢትዮጵያ ብቸኛውን የሜዳልያ ድል ያስመዘገበችው በ1999 እኤአ ላይ የነሐስ ሜዳልያ የወሰደችው ቁጥሬ ዱለቻ  የነበረ ሲሆን ገንዘቤ ዲባባ የወርቅ ሜዳልያ ካገኘች በኋላ ግን በርቀቱ በሴቶቹ ምድብ በዓለም ሻምፒዮናው የተሻለ ውጤት ተመዝግቧል ለማለት ይቻላል፡፡
የመሃመድ  ክብርን የማስጠበቅ ህልም በቴክኒክ ስህተት መበላሸቱ
በ800 ሜትር ወንዶች የመሃመድ አማን ክብር የማስጠበቅ  ከፍተኛ ትንቅንቅ በግማሽ ፍፃሜ  በተፈጠረው ያልተጠበቀ ሁኔታ ተበላሽቶበታል፡፡  በ3 ምድብ በተካሄደው የግማሽ ፍፃሜ ፉክክር በመጀመርያ ዙር ገብቶ የነበረው የወቅቱ ሻምፒዮን መሃመድ አማን በመጨረሻዎቹ ሁለት መቶ ሜትሮች የገጠመው ነገር በወቅቱ ውድድሩን ሲያስተላልፍ በነበረው ኮሜንታተር አገላለፅ እሱን ከመሰለ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው አትሌት የማይጠበቅ ነበር፡፡  መሃመድ አማን የ800 ሜትር ውድድሩ ሊጠናቀቅ በቀሩት የመጨረሻዎቹ ሁለት መቶ ሜትሮች በተፎካካሪ አትሌቶች ከተከበበበት  ሁኔታ ለመውጣት  በግራ በኩል ለማለፍ ያደረገው ሙከራ በሱ እና በሌላ አትሌት ላይ በፈጠረው መደነቃቀፍ ተበላሽቶበታል፡፡
 ሻምፒዮናነቱን የማስጠበቅ እድሉ አጣብቂኝ የገባውም በዚህ ክስተት ነበር፡፡ በሶስቱ የግማሽ ፍፃሜ ማጣርያዎች አንደኛና ሁለተኛ የወጡት በቀጥታ አልፈው መሃመድ አማን በግማሽ ፍፃሜው ያገኘው ፈጣን ሰዓት ከሶስተኛ ደረጃው ጋር በምርጥ ሶስተኛነት ሊያሳልፈው ቢችልም በተሰጠው እድል መሰረት ለፍፃሜ ቢያደርሰውም  ከውድድሩ ውጭ የሆነው በዚያው መደነቃቀፍ ነው፡፡ በኢትዮጵያ የዓለም ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪክ በ800 ሜትር ወንዶች ብቸኛውና  የመጀመርያው የወርቅ ሜዳልያ ድል የተመዘገበው ከሁለት ዓመት በፊት በመሃመድ አማን እንደነበር ይታወሳል፡፡

 የአሜሪካ ሴቶች ከ95 አመታት በፊት የተጎናጸፉት መብት ነው
                   70 ሴቶች በዕጩ ተወዳዳሪነት እንደሚቀርቡ ይጠበቃል
    የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች በመጪው ታህሳስ ወር በሚካሄደው የከተማ አስተዳደር ምርጫ በዕጩ ተወዳዳሪነትና በድምጽ ሰጪነት በመሳተፍ በአገሪቱ በታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የምርጫ ተሳትፎ እድል ተጠቃሚ እንደሆኑ  ሲኤንኤን ዘገበ፡፡በምርጫ ተወዳዳሪነትም ሆነ በመራጭነት የመሳተፍ መብት ተነፍጓቸው የኖሩት የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች፤በታሪካቸው ለመጀመሪያ ጊዜ ካለፈው ቅዳሜ ጀምሮ በመራጭነት እየተመዘገቡ እንደሆነ የጠቆመው ዘገባው፣ ከነገ ጀምሮም በዕጩ ተወዳዳሪነት ይመዘገባሉ ብሏል፡፡የቀድሞው የአገሪቱ መሪ ንጉስ አብደላ የአገሪቱ ሴቶች እ.ኤ.አ ከ2015 ጀምሮ በምርጫ ተወዳዳሪነትና በድምጽ ሰጪነት መሳተፍ እንደሚጀምሩ ከአራት አመታት በፊት ማስታወቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ይሄም ሆኖ ግን ሴቶች ይሳተፉበታል በተባለው ቀጣይ የከተማ አስተዳደር ምርጫ የሚያሸንፉ ሴቶች የተገደበ ስልጣን እንደሚኖራቸው ገልጧል፡፡
በመጪው ምርጫ ሴቶች እንዲሳተፉ መፈቀዱ የአገሪቱን ሴቶች የፖለቲካ ተሳትፎ ተጠቃሚ በማድረግ ረገድ ተስፋ ሰጪ እርምጃ ነው መባሉን ዘገባው ገልጾ፣የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች አሁንም ድረስ ከፍተኛ በደልና ተጽዕኖ እንደሚደርስባቸው ጠቁሟል፡፡
የሳኡዲ አረቢያ መንግስት ሴቶችን የምርጫ ተሳታፊ ለማድረግ መወሰኑ በሴቶች መብት ጥሰት ከፍተኛ ውግዘት ስታደርስበት ከኖረችው አሜሪካ ጋር የተሻለ ግንኙነት እንዲፈጥር በር ሊከፍትለት ይችላል ያለው ዘገባው፣ የአሜሪካ ሴቶች በምርጫ የመሳተፍ መብታቸው የተረጋገጠላቸው ከ95 አመታት በፊት እንደነበር አስታውሷል፡፡በመጪው ምርጫ 70 ያህል የሳኡዲ አረቢያ ሴቶች በዕጩ ተወዳዳሪነት ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅና ሌሎች 80 ሴቶችም በምርጫ ዘመቻ ሃላፊነት ለመስራት መመዝገባቸውን የዘገበው ዴይሊ ሜይል በበኩሉ፣ ይሄም ሆኖ ግን የአገሪቱ ሴቶች አሁንም ድረስ መኪና መንዳት፣ የባንክ ሂሳብ መክፈት፣ ከባላቸው ውጪ ፓስፖርት ማግኘትና ወደፈለጉት አካባቢ መዘዋወር እንደማይፈቀድላቸውና ዘርፈ ብዙ የጾታ ጫና እንደሚደርስባቸው ጠቁሟል፡፡
በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጾታዊ እኩልነት መለኪያ መስፈርት መሰረት፤ ሳኡዲ አረቢያ ከአለማችን 140 አገራት 136ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ዘገባው አክሎ አስታውቋል፡፡

   የጦር ሃይሉ መቀመጫ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ፈጥሯል
    የአረብ ሊግ አባል አገራት የመከላከያ ሚኒስትሮች የጋራ የጦር ሃይል ለማቋቋም የሚያስችላቸውን ስምምነት ከትናንት በስቲያ ለመፈረም ይዘውት የነበረውን ዕቅድ ላልተወሰነ ጊዜ ማራዘማቸውን ኤቢሲ ኒውስ ዘገበ፡፡አባል አገራቱ ግጭት በሚከሰትባቸው አካባቢዎች የሰላም ማስከበር ስራ የሚሰራ የጋራ የጦር ሃይል ለማቋቋም የሚያስችላቸውን ስምምነት ባለፈው ሃሙስ ሊፈርሙ ቀጠሮ ይዘው የነበረ ቢሆንም፣ ሊጉ በዋዜማው ባወጣው መግለጫ እቅዱ ላልተወሰነ ጊዜ መራዘሙን አስታውቋል፡፡አንዳንድ የፖለቲካ ተንታኞች ግን፣ እንደ ሊቢያ ባሉ አገራት መንግስትን ለሚቃወሙ ሃይሎች ድጋፍ የሚሰጡ የአረብ አገራት ባሉበት ሁኔታ፣ የሚያቋቁሙት የጋራ የጦር ሃይል ጣልቃ ይግባ አይግባ የሚለው ጉዳይ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ሊፈጥር ይችላል ማለታቸውንም ዘገባው ጠቁሟል፡፡ የጦር ሃይሉ መቀመጫ የሊጉ ዋና ጽህፈት ቤት በሚገኝባት ካይሮ ይሁን የሚለው ሃሳብ በአገራቱ መካከል አለመግባባት ፈጥሮ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ስምምነቱ የተራዘመው ሳኡዲ አረቢያ፣ ባህሬን፣ ኩዌት፣ ኳታር፣ የተባበሩት አረብ ኢሜሬትስና ኢራቅ ባቀረቡት ጥያቄ መሰረት መሆኑንም ገልጧል፡፡አገራቱ የጦር ሃይሉን ለማቋቋም ፈቃደኛ መሆናቸውን ባለፈው መጋቢት ወር በይፋ ማስታወቃቸውንና በግንቦትም ስምምነቱን ማርቀቃቸውን ዘገባው አስታውሶ፣የተራዘመው ስምምነት የሚፈረምበትን ቀን አገራቱ ወስነው እንደሚያስታውቁ ጠቁሟል፡፡