Administrator

Administrator

የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ፓርቲ ዋና ጸሐፊ በመሆን ለአስር አመታት ያገለገለው አቶ ማሙሸት አማረ “በፓርቲው ህልውና ላይ ጉዳት አድርሰሀል” በመባል እሱን ጨምሮ 17 የፓርቲው አመራሮች ከፓርቲው የታገዱት የዛሬ ሁለት ዓመት ገደማ ነው፡፡ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት በመውሰድ ሲከራከሩ የነበሩት እነ ማሙሸት አማረ እና እነ ኢንጂነር ሃይሉ ሻውል ሲሆኑ ፍ/ቤቱም ተከሳሽ የነበሩ እነ ማሙሸት “ምንም አይነት ሁከት አልፈጠሩም” በማለት ወደ ፓርቲው እንዲመለሱ መስጠቱ ይታወሳል። ሆናም ትዕዛዙ ተግባራዊ ሳይሆን አንድ ዓመት አልፎታል፡፡ “ፓርቲው ውስጣዊ ችግሮች አሉበት” በማለት የሚናገሩት እነ አቶ ማሙሸት፤ ዛሬ የፓርቲውን ችግር በውይይት ለመፍታትና “ጠቅላላ ጉባኤ ይጠራ” በማለት ከምርጫ ቦርድና ከኢንጂነር ኃይሉ ሻውል ጋር እየተነጋገሩ ነው፡፡ ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው በእነዚህ ጉዳዮች ዙሪያ አቶ ማሙሸት አማረን አነጋግራለች፡፡

ከመኢአድ ከታገድክ ስንት ጊዜ ሆነህ?

በ2003 ዓ.ም በተደረገ ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ነው የዚህ ፓርቲ ዋና ፀሐፊ በመሆን የተመረጥኩት። ከዚያ በኋላ ነው የታገድኩት፡፡ በአቶ ሃይሉና በአቶ ያዕቆብ ከፓርቲው ውጪ በሄደ ደንብ የውስጥ አለመግባባት ተፈጥሮ አቶ ኃይሉ ጉዳዩን ወደ ፍ/ቤት ወስዶ ክርክር ከተደረገበት በኋላ ፍ/ቤቱ የተከሰስንበት ጉዳይ ስህተት መሆኑን አውቆ ወደ ፓርቲያችን እንድንመለስና ጠቅላላ ጉባኤው ተሰብስቦ የመጨረሻ እልባት እንዲሰጥ ተወሰነ፡፡ ከሳሾች ፍ/ቤቱ ትክክል አልፈረደም ብለው ለከፍተኛ ፍ/ቤት ይግባኝ ጠይቀው ነበር፡፡ ሆኖም ፍ/ቤቱ የስር ፍ/ቤትን ውሳኔ አጸና፡፡ አቶ ሀይሉና ሌሎቹ ግን የችሎቱን ትዕዛዝ ማክበር ባለመቻላቸው፣ ምርጫ ቦርድ ውሳኔውን እንዲያስፈጽም ትዕዛዝ ሰጠልኝ፡፡ ቦርዱም ይህንን መነሻ በማድረግ ለአቶ ሃይሉ በ2004 ዓ.ም ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠሩ ትዕዛዝ ቢሰጥም ጉባኤው ሳይጠራ ቀረ፡፡ እኛም ትግላችንን በህጋዊ መንገድ በመቀጠል ያላሰለሰ ጥረት አደረግን፡፡ ይኼም ተቀባይነት ሊያገኝ አልቻለም፡፡ እንግዲህ እንደምንሰማው አቶ ሃይሉ “አባረናል አጥርተናል” ይላሉ፡፡ ሆኖም እሳቸው የማባረርም የማጽዳትም ስልጣን የላቸውም፡፡

የመኢአድ አባል ስትሆን ምኑን መርጠህ ነው?

ከ1984 ሚያዚያ 15 ጀምሮ መ.አ.ህ.ድ ነበርኩ። ኢህአዴግ ከገባ በኋላ በአማራው ተወላጅ ላይ በየክልሉ ከፍተኛ በደል ሲያደርግ ይሄ በደል ይቁም በማለት በዚህ እንቅስቃሴ ለመሳተፍ ነው አባል የሆንኩት፡፡ ከዚህ በኋላ የታገልንለት ህዝብ ለምን ለአማራው ብቻ ትታገላለችሁ ሁሉም ብሔሮች ችግር እየደረሰባቸው ነው ያሉት፤ ለምን ለሁሉም ብሔር አትታገሉም የሚል ከፍተኛ አስተያየት በመኖሩ አባላቱ በሰጡት ውሳኔ መሠረት በ1995 ዓ.ም መአህድ ወደ መኢአድ ተቀየረ፡፡ መአህድ ወደ መኢአድ ከተቀየረ 10 አመት ሆኖታል፡፡ በዚህ ጊዜ የፕሬዚዳንቱን ችግር አታውቁም ነበር? በዚህ ፓርቲ ውስጥ በርካታ ችግሮች ይታዩ ነበር፡፡ ነገር ግን የሚፈቱት በውይይት ነበር፡፡ አንድ ሰው ችግር አለበት ተብሎ ከታሰበ ውይይት ላይ ይቀርባል፡፡ ያ ውይይት የቀረበበት አጀንዳ፣ የፓርቲው ስራ አስፈፃሚ በጊዜያዊነት ያግድና ለላዕላይ ምክር ቤት ያቀርባል፡፡ ም/ቤቱም ያይና የመጨረሻ ውሳኔ በመስጠት በጠቅላላ ጉባኤ ላይ ያሳውቃል፡፡ የእኛ መታገድ ግን ከዚህ የተለየ ነበር፤ በፕሬዚዳንቱ ደብዳቤ ብቻ ነው “ሁከት ፈጥራችኋል” ተብለን ወደ ፍ/ቤት የሄድነው መጀመሪያም ወደ ፍ/ቤት የሄድነው ያለ አግባብና ከመተዳደሪያ ደንቡ ውጪ ነው፡፡ በመተዳደሪያ ደንቡ መሠረት ሄደው ሳይሳካ ሲቀር ነው ፍ/ቤት የሚኬደው፡፡ ሌሎች በህገደንቡ መሠረት ከፓርቲው ከታገዱና ከተሰናበቱ ለምን እናንተ በህገወጥ መንገድ ሆነ ትላላችሁ?

እኛ ያቀረብነው መከራከሪያ ሃሳብ ትክክለኛ መረጃ ይዘን ነው፡፡ ለምሳሌ ከታህሳስ 15-17 2003 ዓ.ም በተካሄደ ጠቅላላ ጉባኤ፣ አቶ ሃይሉ አቶ ያዕቆብን ከመተዳደሪያ ደንቡ ውጭ ተቀዳሚ ሊቀመንበር አድርጌ ሾሜዎአለሁ አሉ፤ እሳቸው ይህንን ማድረግ አይችሉም፡፡ እሳቸው የሚችሉት ከሌላ ስራ አስፈፃሚዎች ጋር ሆነው ሌላ ስራ አስፈፃሚ የሚሆኑትን በመምረጥ ለላይዕላይ ም/ቤት ያቀርባሉ፤ ላዕላይ ም/ቤቱ ነው የሚያፀድቀው፡፡ ይኸ ሹመት ነው፡፡ በሊበራል ስርዓት በአንድ ግለሰብ የሚመረጥ ሹመት የሚባል ነገር የለም፡፡ በምርጫ ነው የሚደረገው፤ ባላቸው የስራ ልምድና የትምህርት ሁኔታ ነው፡፡ በዚህ ከተመረጠ ያልፋል፡፡ ካልተመረጠ ይወድቃል፡፡ እሳቸው ግን ቀጥታ አምጥተው አቶ ያዕቆብን ተቀዳሚ ሊቀመንበር አድርገው ሾሙ፡፡ ይሄ ነው ችግሩ፡፡ አንደኛ አቶ ያዕቆብ የድርጅቱ አባል አልነበሩም፡፡ የዕለቱ ዕለት ነው ለላዕላይ ም/ቤት ቀርቦ አባል ነው የተባለው፤ ዛሬ አባልነቱ ቀርቦ ወዲያውኑ ፕሬዚዳንት የሚሆንበትን ስርዓት ደንባችን አይፈቅድም፡፡ ይሄ ታዲያ በአቶ ሃይሉ ዘንድ እንደቂም ተወሰደ፡፡ እንዴት እኔ የምለውን አያከብሩም ብለው ተቆጡ፡፡ እኛ ደግሞ ማንም ከመተዳደሪያ ደንባችን ውጭ ከሆነ ስለምንታገል፤ ዋና አላማችንም ይሄ ስለሆነ እስከ መጨረሻው ፀንተናል፡፡ አቶ ሃይሉ አንድ አባልን ማገድ እንኳን የሚችሉት ለሁለት ወር ጊዜ ብቻ ነው፡፡ እኛ ደግሞ አመራሮች ነን፤ በእሳቸው ልንታገድ አንችልም፡፡ ወሳኙ ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤው ነው፡፡ ከ105 የላዕላይ ም/ቤት ውስጥ በተለያዩ ችግሮች 82 ሲቀሩ፣ ከነዚህ ውስጥ 57 የሚሆኑት አባላት ከእኛ ጋር ናቸው፡፡ ስለዚህ ይሄንን ሃሳባቸውን ለም/ቤቱ አቅርበው የሚያፀድቅላቸው ስለሌለ ነው አኩርፈው የተቀመጡት፡፡ አሁንም ለመነጋገር የማይፈልጉትም ለዚህ ነው፡፡ አሁንም “በውይይት እንፍታ ሲባሉ አልፈልግም” ያሉት ለዚህ ነው፡፡ የተቃወምነውን ትክክል ነው ብለን ሲቃወሙን ከቆዩ በኋላ አቶ ያዕቆብን በደብዳቤ አባረዋል፡፡ እናንተ በፓርቲው ውስጥ አመራር በነበራችሁ ጊዜ የኢንጂነር ኃይሉ ተቀናቃኞች ኢንጂነሩ ስልጣናቸውን ይልቀቁ ይሉዋችሁ ነበር፡፡

እናንተ ይሄን ችግር በወቅቱ አታውቁም ነበር?

ሌሎች ከፓርቲው ወጥተው ነገሩን ይተውታል አሊያም ሌላ ፓርቲ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ይሄ ደግሞ ቅልውጥና ነው፤ ሌላ ነገር አይደለም፤ ማንም የፖለቲካ ሰው ላሰበበት ዓላማ መሳካት እስከመጨረሻው መታገል አለበት፡፡ አንድም አባል ግን እኛን ይሄንን ችግር አደረሳችሁብኝ ብሎ አጀንዳ ያስያዘ የለም፡፡ የመጀመሪያው እኔ ነኝ፡፡ እኛን ብዙ ጊዜ ሲሰድቡን አውቃለሁ፡፡ እኔ ግን ለግለሰብ አጐብድጄአለሁ፡፡ በፍፁም ሌሎቹ በጭቆና አይደለም የሚወጡት፡፡ እኛ ብቻ ነን በጭቆና የታገድነው፤ ስለዚህ እስከዚያ ድረስ በፓርቲው ውስጥ ትልቅ ችግር የሚባል አልነበረም፡፡ የእናንተ ቅሬታ ኢንጂነር ኃይሉ አቶ ያዕቆብን በመሾማቸው ነው፡፡

ኢንጂነር ሃይሉ እንዲመረጡ ደግሞ አንተ በአባላቱ ላይ ግፊት አድርገሃል፡፡ ታዲያ አሁን ለምን ችግር አለ ትላለህ?

በመጀመሪያ አቶ ያዕቆብ በምርጫ ባለመመረጣቸው ነው ቅሬታ ያቀረብነው፡፡ አቶ ያዕቆብን ያመጡዋቸውም አቶ ሃይሉ ናቸው፡፡ ይሄ ስንቃወም ስልጣን ፈልጋችሁ ነው ተብለናል፡፡ ከ400 በላይ ለሆኑ የጠቅላላ ጉባኤ አባላት አቶ ሃይሉን ምረጡ ብዬ የቀሰቀስኩት እኔ ነኝ፡፡ በዛን ሰአት እኔን ምረጡኝ ማለት እችል ነበር፡፡

ለምን ኢንጂነር ሃይሉ እንዲመረጡ አደረግህ?

ፓርቲው ላይ ትንሽ ችግር ነበር፡፡ አቶ ሃይሉ ለስምንት ወራት ከ2002 ምርጫ በኋላ ወደ ፓርቲው አልመጡም፡፡ ለዶ/ር ታዲዮስ ውክልና ሰጥተው ነበር የሚፈረመው፡፡ ጠቅላላው ጉባኤው ይጠራ ብለን ወጥረን ስንይዝ፣ አቶ ያዕቆብ ጠቅላላ ጉባኤ እንዲጠራ አልፈለጉም፡፡ ምክንያቱ ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤው አቶ ያዕቆብን አያውቃቸውም፡፡ በዚህ መሃል አቶ ኃይሉ ወደ ቢሮ እንዲመለሱ አቶ ያዕቆብ ግፊት እያደረጉ ነበር፡፡ አንተ ለአባላቱ ከነገርክልኝ ልመረጥ እችላለሁ ማለታቸውን ያወቅነው ከጠ/ጉባኤ አባላቱ ሲወጡ “እንዲህ እየተባልን ነው፤ አቶ ሃይሉ ደውለው አቶ ያዕቆብን ምረጡ እያሉን ነው” የሚል ነገር ነገሩን፡፡ የላዕላይ ም/ቤቱ የሚያቀርብላችሁን ሰው እጃችሁን አውጥታችሁ ስትመርጡ ነው እንጂ በጐን እየተደወለ ምረጡ ስለተባላችሁ ብትመርጡ አይሆንም አልን፡፡ ስለዚህ እንደዚህ አይነት ችግር ከመጣ ሠላማዊ ሽግግር ስለሚያስፈልግ ተብሎ አቶ ሃይሉ ይሄንን ፓርቲ ለስድስት ወር መምራት አለባቸው በሚል የጠቅላላ ጉባኤውን አባላት ምርጫችሁ ኢንጂነር ሃይሉ መሆን አለበት ብያቸው ነበር፡፡ ሁሉም በደስታ ተቀብለው የተባሉትን አደረጉ፡፡ እሳቸውም መድረክ ላይ ወጡና ደከመኝ ስል አልሰማም ብላችሁ እኔን መርጣችኋል፤ ስለዚህ እኔን እንዲያግዙኝ አቶ ያዕቆብ ልኬን ወክያለሁ ሲሉ ችግር ተፈጠረ፡፡

ችግር የፈጠሩት ኢንጂነር ሃይሉ ናቸው እያላችሁ ነው፤ ቀድማችሁ አቶ ያዕቆብን ምረጡ ማለታቸውንም ታውቃላችሁ፡፡ ይሄንን እያወቃችሁ ለምን እንዲመረጡ ፈለጋችሁ?

ጠቅላላ ጉባኤ የምንጠራበት ጊዜ ሊያልፍብን በመሆኑ ሳያልፍ ነበር ለማካሄድ ያስፈለገው። በወቅቱ ደግሞ ለፕሬዚዳንትነት የተሾመ ሰው አልነበረም፡፡ ስለዚህ አቶ ሃይሉን ስንመርጥ በህመምና በመሰልቸት ምክንያት ቤታቸው ቀሩ ብለን አስበን እንጂ እንዲህ አይነት ተንኮል ለማድረግ አስበዋል ብለን አልገመትንም። ይሄንንም የሰማነው አባላቱ ተጠቃለው አዲስ አበባ ከገቡ በኋላ ነው፡፡ ችግር እየፈጠሩ መሆናቸውን የሰማኸው ጠቅላላ ጉባኤው ሊካሄድ ሁለት ቀን ሲቀረው ነው ብለሃል። ነገር ግን ችግሩን ከመፍታት ይልቅ መልሳችሁ እሳቸውን መርጣችኋል፡፡ አሁን ደግሞ ችግር ፈጠሩ እያላችሁ ነው፡፡ ሌሎች ደግሞ ማሙሸት እራሱን በአቶ ያዕቆብ ቦታ ለመተካት አስቦ ስለነበር ነው ይላሉ… ይሄ ከእውነት የራቀ የሞኞች ሃሳብ ነው። እኔ የስልጣን ጥም የለብኝም፡፡ ብፈልግ ደግሞ እኔ እራሴን አስመርጥ ነበር እንጂ አቶ ሃይሉን አላስመርጥም ነበር። ይሄንን ለማድረግ ለእኔ ቀላል ነው፡፡

አቶ ያዕቆብ ለጠቅላላ ጉባኤ ምርጫ በዕጩነት ባለመቅረባቸው ነው ችግራችሁ ወይስ ሙሉ በሙሉ ለዕጩነት መቅረብ አይችሉም ነው ተቃውሟችሁ?

አቶ ያዕቆብ አይደለም ለአመራርነት ለፓርቲ አባልነትም አይበቁም፡፡ በጣም ችኩል ናቸው። የቆዩትም በብዙ ችግር ነው፡፡ አቶ ያዕቆብ የፓርቲ አባል ሆነው አያውቁም፡፡ ዛሬ ጠዋት የመኢአድ የላይላይ ም/ቤት አባል ሆነው፣ ነገ ደግሞ ስራ አስፈፃሚ ሆነው መሾም አይችሉም፡፡ ደንቡም አይፈቅድም፡፡ ሌላው ደግሞ አቶ ሃይሉ መሾም አይችሉም፤ ይሄ የአልጋ ወራሽነት አሠራር አይደለም። እሳቸው ትልቅ ጂም ሠርተዋል፤ ከፈለጉ የዚያ ሃላፊ ሊያደርጓቸው ይችላሉ።

አቶ ያዕቆብ እንዲመረጡ ካልፈለጋችሁ ኢ/ር ሃይሉ ደከመኝ እያሉ ከምትመርጡ ለምን ፓርቲው በም/ፕሬዚዳንቱ እንዲመራ አላደረጋችሁም?

እኛም ያንን ነበር የጠበቅነው፤ ከደከማቸው ለሌላኛው ም/ፕሬዚዳንት መስጠት ይችላሉ፤ ያንን ባለማድረጋቸው እና አባል ላልሆነ ሰው ስልጣን በመስጠታቸው ነው ትልቁ ችግራችን፡፡ ካላወቁት መልአክ የሚያውቁት ሰይጣን ይሻላል ነው የሚለው ቃሉ፡፡ ከፓርቲው ከተለያችሁ ሁለት አመት ሆኗችኋል።

በዚህ ጊዜ ምን ሠራችሁ? የጠ/ጉባኤ ጥሪያችሁ ምን ይመስላል?

ፓርቲን የማደራጀት ስራ ነው እየሰራን የቆየነው፡፡ ፓርቲያችንን ለማንቃት እየሰራን ነው፡፡ 320 የሚሆኑ የፓርቲው ጠቅላላ ጉባኤ አባላት ፈርመው ለምርጫ ቦርድም አስገብተዋል ግን እስካሁን የተወሰነ ነገር የለም፡፡ እናንተ የምትጠይቁትን ነገር ኢንጂነር አልቀበልም ቢሉስ? የፓርቲው አባላት ይሰበሰባሉ፤ ውይይት ያደርጋሉ። ከዚያም ሁለት አመት ሙሉ የሔደበትን ለዚህ አጣሪ ጉባኤ ሪፖርት ያቀርባል፡፡ ስራ የሰራም ከሆነ የሰራውን፣ ያልሠራም ከሆነ ያልሠራበትን፤ ችግሮች ካሉ ችግሮቹን በሙሉ ያቀርብና ምርጫ ይካሄዳል፡፡ ከዚያ ከአምስት እጩዎች ውስጥ አንድ ለፕሬዚዳንትነት፣ ሌሎቹ ለምክትል ፕሬዚዳንትነት ይቀርባሉ፡፡ አቶ ሃይሉ በዚያ ጠቅላላ ጉባኤ ካልተመረጡ ውድቅ ይሆናሉ፡፡ ቦርዱም እውቅና እሚሰጠው በዚያን ጊዜ ለተመረጡት ፕሬዚዳንት እንጂ ለሌላ አይደለም፡፡ እለቃለሁ ስላሉ አይለቁም፤ አልለቅም ስላሉም አይቆዩም፡፡

አብዛኞቹ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና አመራሮች ስለፓርቲያቸውና ስለአባላት ድክመት የሚናገሩት ፓርቲያቸውን ከለቀቁ በኋላ ነው፡፡ “ለምን በፓርቲው ውስጥ እያሉ ስለችግሮቻቸው አይናገሩም?” በሚለው ዙሪያ በቅርቡ ከአንድነት ፓርቲ የለቀቁት ኢንጂነር ዘለቀ ረዲን ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው አነጋግራለች፡፡

በአንድነት ፓርቲ ውስጥ ለምን ያህል ጊዜ ቆዩ?

አንድ አመት ከስምንት ወር ይሆነኛል፡፡ የ “ብርሃን ለአንድነትና ለዲሞክራሲ ፓርቲ” መስራች ነበርኩ፡፡ በዛን ሠአት ነው የመበታተን ፖለቲካ ለአገሪቱ ስለማይጠቅም በሚል ለተቃዋሚ ፓርቲዎች ደብዳቤ ያስገባነው፡፡ በጋራ ለመስራት ማለት ነው። አንድነትና መኢአድ ጥያቄያችንን የተቀበሉን ሲሆን መኢአድ ግን “አንድነት” ከመድረክ ካልወጣ የሚል ጥያቄ አቀረበ፡፡ ይሄኔ “አንድነት”ም ብዙ ዋጋ የከፈልኩበት ነው በሚል አልወጣም አለ፡፡ እኛም በዛ ተስማምተን በጋራ ለመስራት ተቀላቀልን፡፡ በፓርቲው ውስጥ ችግር እንዳለ የገለፁት ከአንድነት ከወጡ በኋላ ነው፡፡ ከዛ በፊት ለምን አልተናገሩም? እኔ ችግሮች እንዳሉ በስብሠባ ላይ እገልፃለሁ። በፅሁፌም እናገራለሁ፡፡ እኔ ነጋዴ ነኝ፡፡ ፓርቲ ውስጥ የገባሁት ለለውጥ ነው፤ ስለ ድክመቱ ሁሌም በፅሁፍ እተቻለሁ፡፡ ለውጥ እንዲመጣ ነው ቤተሠቤንና ጊዜዬን መስዋዕት አድርጌ እየሠራሁ ያለሁት፡፡

ከመፃፍህ ባለፈ ለሚዲያ አሁን እንደተናገርከው የገለፅከው የፓርቲው ችግሮች አሉ?

ከሌሉ አሁን መግለፁ ለምን አስፈለገ? አጠቃላይ ችግሮቻችንን በቃለ ጉባኤ አስይዤ አውቃለሁ፡፡ ለምሳሌ አንዳንድ ሠዎች “አቶ አስራት ሴረኛ ናቸው” ሲሉ ሴራውን አብራራው ብዬ እከራከራለሁ፡፡ አንድ ሠው ሴረኛ ነው የምለው” ፓርቲው እንዳያድግ ወደታች የሚያደርግ እና ብቻውን ጐልቶ ለመታየት የሚፈልግ ከሆነ ነው፡፡ አንድ የፖለቲካ ፓርቲ መሪ፤ መንገድ ጠራጊ ዶዘር እንጂ እራሱን ለማሳየት የሚጥር መሆን የለበትም፡፡ ስራዎች እንዳይሠሩ ወይም ከፓርቲው መውጣት የሚፈልጉ ሠዎች እንዳይወጡ መሰናክል የምትፈጥሪ ከሆነ፣ ይሔ ነው ሴራ ማለት፡፡ ቁጭ ብለሽ ነገር ትጐነጉኛለሽ አትወጪም፤ ሊወጡ የሚፈልጉትን ደግሞ ነገር እየፈለግሽ ስስ ብልታቸውን በመምታት ብሎናቸውን ፈተሽ እንዲወድቁ ታደርጊያለሽ። ይሔንን በሚዲያ ከመናገር ይልቅ በውይይት ይፈታል ብዬ ስላሠብኩ ችዬው ኖርኩ፡፡ አሁን ግን ወቅቱ በመሆኑ ተናግሬያለሁ፡፡ እስቲ ሴራ ስለሚሉት ጉዳይ ያብራሩልኝ … ሰሜን ጐንደርን እኔ ስረከበው ለሁለት የተከፈለ ቡድን ነበር፡፡ ያንን ለማስታረቅ ከሠባት ጊዜ በላይ በአውሮፕላንና በመኪና ተጉዘናል፡፡ ግን ሊታረቁ አልቻሉም፡፡ ይሔም የሆነው ደግሞ አቶ አስራት በሠሩት ሴራ ነው፡፡ በመሀል ገብተው አንደኛውን ቡድን በማቅረብ፣ ሌላኛውን ቡድን በማራቃቸው ችግሩን መፍታት አልቻሉም፡፡ እኛ ስንገባበት ደግሞ ችግሩን ለመፍታት የሚያስፈልግ ገንዘብ እንዳይወጣ አቶ አስራት ከለከለ፡፡

\ስለዚህ ከእኔና ከሌሎች ስራ አስፈፃሚዎች ገንዘብ ተወስዶ፣ ልጆቹ ፆማቸውን እያደሩ ችግሩ በንግግር ተፈታ፡፡ አጣዬ የምትባል ቦታም ተመሳሳይ ችግር ተፈጥሮ ነበር፡፡ እኛ ግጭታችን ከፓርቲ ጋር ነው እንጂ የድንበር ግጭት አሊያም ሌላ የግል ግጭት የለብንም፡፡ በፊት ፓርቲው ለእንደዚህ አይነት ችግሮችና ለአባላት ስልጠና ገንዘብ መድቦ ይንቀሳቅስ ነበር፡፡ ልክ እኔ ስመጣ ገንዘቡን ከለከሉ፤ ምክንያቱ ደግሞ ሽባ እንድሆን ስለፈለጉ ነው፡፡ በእኛ እድሜ ያሉት ስራ እንዲሠሩ አይፈለግም፡፡ ስለዚህ ብሩን ከልክለው “ይሔው መስራት አልቻሉም” ለማለት ይፈልጋሉ፡፡ እናም “ፓርቲው ችግር ላይ ነው” ብዬ ሠዎችን አግባብቼ፣ ሠሌን ላይ እያደሩ ነው ስልጠና ወስደው ሀያ አምስት ቢሮዎች የከፈትኩት፡፡ ይሔ ሀቅ ነው፡፡ መተዳደሪያ ደንቡን በራሴ ወጪ ወደ ኦሮምኛ አስተርጉሜያለሁ፡፡ አሁን በፍኖተ ነፃነት ዌብሳይት ላይ የለቀቁት ነገር አለ፡፡ እኔ ኢህአዴግ እንደሆንኩ ገልፀዋል፡፡ ይሔን ጊዜ ይፈታዋል፡፡

ፓርቲው እንደ ኢህአዴግ እየሠራ ከሆነ ኢህአዴግ ነው ማለት ነው፡፡ ፓርቲው በርካታ የበሠሉና በእውቀት ያደጉ አባላቶችን የያዘ ነው፡፡ አመራሮቹ ግን በጣም ደካማ ናቸው፡፡ የፓርቲው አባላት በደንብ ቢሠራ ለውጥ የሚያመጡ ናቸው። ምንም ሳይሠራ ነው 25 ቢሮዎች የከፈትነው፡፡ ግን ፓርቲው እንዳያድግ የሚያደርጉ አመራሮች ናቸው። አመራሮቹ እኮ ስብሠባ ተከለከልን ብለው ዝም ብለው ይቀመጣሉ፡፡ ኢህአዴግ እስኪፈቅድ ነው የሚጠብቁት?

ከሆነስ መቼ ነው የሚፈቅድልን? እኔ በበኩሌ በየኤምባሲው እየሔዱ እንደራደር ማለታቸውን በፍፁም አልፈልገውም፡፡ የፓርቲውን ክብር ይነካል፡፡ ኢህአዴግ እራሱ እንዲደራደረን ነው መጥራት ያለብን እንጂ እኛ መሔድ የለብንም። ይሔ ከሴረኝነት የሚተናነስ አይደለም፤ ፓርቲውን ቁልቁል ይሰደዋል እንጂ አያሳድገውም፡፡ እኔ አሁንም ፓርቲውን አለቅም በአባልነት እቀጥላለሁ፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲ ማለት እኮ ሌላ መግስት ነው፡፡ ሌላ አገር ያሉት እኮ ይፈራሉ እንጂ ልመና አይገቡም፡፡ እዚህ ግን ሴራቸው ሲጋለጥ ይቆጣሉ፤ እኔ ደግሞ ውስጣቸውን ሸፍኜ የትውልድ ተወቃሽ መሆን አልፈልግም፡፡ የመልቀቂያ ደብዳቤ አስገብተህ ነው የወጣኸው? እኔ ህጋዊ መልቀቂያ አስገብቼ ነው የለቀቅሁት። እነሱ ቀንና ቁጥር የሌለው ደብዳቤ ሠጠን ይላሉ። መቼም ይሔን የሚያክል ፓርቲ የሚያስተዳድርና አስቀድሞ አገርን ይመሩ የነበሩ መሪ ደብዳቤ ሲወስዱ ቀንና ቁጥር አይተው ነው የሚሆነው፤ ግን እንደ ምክንያት ያወሩታል፡፡

አንዳንድ ሠዎች ንግግርህን ብታሳምረው ይላሉ፡፡ እኔ ግን አካፋን አካፋ፣ ዶማን ዶማ ማለት ነው የምፈልገው፡፡ ኢህአዴግ እነ አንዷለም አራጌ ስለ ነፃነት ሲናገሩ ግንቦት ሠባት አላቸው፡፡ አንድ ሠው ስለ አማራ ሲናገር፣ ነፍጠኛ፤ ስለ ኦሮሞ ሲናገር ደግሞ ኦነግ እያለ ኢህአዴግ ስም ይሠጣል፡፡ እነዚህ ደግሞ ሀሳቡን በነፃነት የተናገረንና ችግራቸውን የገለፀ ሠው ኢህአዴግ ነው ይላሉ፡፡ እንደውም ዶ/ር ነጋሶ ናቸው ኢህአዴግነታቸውን ይዘው የመጡት። ምክንያቱም የመናገር ነፃነታችንን እየነፈጉን ነው ያሉት፡፡ ለምሳሌ ፍኖተ ነፃነት ስለ እኔ የተሳሳተ ነገር በዌብሳይቷ ይዛ ወጥታለች፡፡ ታዲያ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ በምን ለይቼ አያታለሁ፡፡ አዲስ ዘመን የአቶ ሀይለማርያምን ሃሳብ ይዞ ከወጣ በኋላ፣ የእኛን ግን አያወጣም፡፡ ፍኖተ ነፃነትም እያደረገ ያለው እንደዛ ነው፡፡ ችግሮችን ከፓርቲ ወጥቶ ከማውራት ለመፍታት መሞከር አሊያም ከወጡ አለመናገሩ አይሻልም? ለትውልድ እዳ ማስቀመጥ አልፈልግም። ለህዝብም ግልፅ ነገር ተናግሬ ነው መልቀቅ የምፈልገው፡፡ ከእኔ ብዙ ነገሮች የሚጠብቁ ሠዎች ይኖራሉ፡፡ ስለዚህ ችግሮቹን ለመፍታት ጥረት አደርጋለሁ፡፡ አልሳካም ካለኝ ደግሞ ችግሩን ለሚዲያ እናገራለሁ፡፡ ለምሳሌ ዶ/ር ነጋሶን እንውሠድ ዶ/ር ናቸው፡፡

ፒኤች ዲ የሚኮነው ከመሬት ተነስቶ አይደለም፤ የፊሎሶፊ ዶክተር ናቸው፡፡ አንድ እንደ እኔ በእድሜና በትምህርት የሚያንሳቸውን አርቅቆ ሠው ማድረግ መቻል አለባቸው፤ እሳቸዉ ግን እንዲማር ሳይሆን እንዲማረር ነው የሚያደርጉት። አንድ ሠው አንድ መፅሔት ላይ ስለ እኔ ፅፏል፡፡ በትልቅነታቸው ቢያከብራቸው ብሏል፤ ነገር ግን ፖለቲካ ላይ ሽማግሌ ብሎ ነገር የለም፤ እንደዚህ ያለው ነገር የሚሰራው ሠፈርና እድር ውስጥ ብቻ ነው፡፡ አብዛኞቻችን እኮ አገራችንን አንወድም። እዚህ አርግዘን አሜሪካን ወልደን ለመምጣት የምንፈልግ ነን፡፡ ሌሎቹ እኮ እዚህ አርግዘው ለመውለድ አገራቸው ነው የሚሔዱት፡፡ ለፓርቲው አድርጌለታለሁ የሚሉት ነገር ምንድነው? በገንዘብም በጉልበትም ብዙ ነገር አድርጌለታለሁ። ይሔንን መጥቀስ አያስፈልግም።

ዶ/ር ነጋሶ ለጀርመን ሬድዮ ሲናገሩ ገንዘቡን እንደፈለገ ሊረጨው ስለፈለገ ነው ብለዋል፡፡ እኔ ገንዘቡን ብረጨውና አባላቱ ከመጡ፣ እሳቸው የሚፈልጉት ይሔንን አይደለም እንዴ? ግን ያልሆነ ያልተደረገ ነገር ሲወራ ያሳዝናል፡፡ ፓርቲውን ቢመራው ብለው የሚያስቡት ማንን ነው? አቶ ተክሌ የፋይናንስ ሀላፊ ናቸው፡፡ እሳቸው ቢመሩት ከፍተኛ ለውጥ እንደሚመጣና የተሻለ ስራ እንደሚሠሩ አምናለሁ፡፡ ከዚህ በኋላስ ምን ለማድረግ አስበዋል? ፓርቲዬን አልተውም፤ በአባልነት እቀጥልላለሁ። እንደዚህ አይነት አመራሮች ፓርቲውን እንዳያሽመደምዱት የበኩሌን እጥራለሁ፡፡

የኛ ምኞት ጉዳዩ በሲኖዶስ ደረጃ እንዲታይ ነው

ቅዱስ ኤልያስ ሥልጣን፣ ሃብትና ንብረት አይፈልግም

አልመጣም ብንለውም መጥቷል ብንለውም የምንቀይረው ነገር የለም

ልቦናው ንፁህ ለሆነና እግዚአብሔር ለፈቀደለት ሰው በአካል ይታያል

ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን አባል የሆነችበት “ማህበረ ስላሴ ዘደቂቀ ኤልያስ” የተባለው የጽዋ ማህበር አነጋጋሪ እየሆነ መምጣቱ ይታወቃል፡፡ ማህበሩ ከኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስያሜ አንስቶ መስተካከል ያስፈልጋቸዋል የሚላቸውን ጉዳዮች በይፋ እየገለፀ ነው፡፡ ከሁሉም በላይ የውዝግብ መነሻ የሆነው ግን ቅዱስ ኤልያስ ወደ ምድር ወርዷል ማለቱ ነው። ይህን ትምህርት በስፋት የሚሰጡት ደግሞ አባ ዮሴፍ ብርሃነ ናቸው። አባ ዮሴፍ ብርሃነ በ1984 ዓ.ም ከ4 ኪሎ ዩኒቨርስቲ በፊዚክስ ዲፓርትመንት በዲግሪ ከተመረቁ በኋላ ስለሃይማኖት መማር ስለሚፈልጉ፣ ድግሪያቸውን ስራ ሳይፈልጉበት አስቀምጠውት ደብረ ሊባኖስ ገብተው የቆሎ ትምህርት ተምረው በማጠናቀቅ ለ12 አመታት በጐንደርና በጐጃም ያገለገሉ ሲሆን በ2000 ዓ.ም የካቲት ወር ላይ በቀጥታ ወደ ማህበረ ስላሴ በመምጣት ማስተማር የጀመሩ ናቸው። እንዲሁም ጃማይካ ሁለት ጊዜ ሄደው ገዳም ገድመው የተመለሱ የሃይማኖት አባት ከእነዚህ አነጋጋሪ አጀንዳ ይዘው ብቅ ካሉ የማህበሩ አባላትና ከአባ ዮሴፍ ብርሃነ ጋር የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የማህበሩ አባል በሆኑት በፕሮፌሰር ይስማው አለሙ መኖሪያ ቤት የተለያዩ ጥያቄዎችን ይዞ በመቅረብ ተነጋግሯል፡፡

ኤልያስ ወርዷል እያላችሁ ነው፤ ማነው ኤልያስ?

የትስ ነው ያለው?

ይሄን ጥያቄ ከመመለሴ በፊት አንድ ነጥብ ላንሳ፡፡ ይሄ ማህበር የት የት ተሰብስቧል፤ የት ጉባኤ አድርጓል የሚለውን ካነሳን፣ በእርግጥም “ማህበረ ስላሴ ዘደቂቃ ኤልያስ” ስፍር ቁጥር በሌላቸው ገዳማትና አድባራት ጉባኤ አካሂዷል፡፡ የቅዱስ ኤልያስን መውረድ ለብዙ እልፍ አዕላፍ ምዕመናን ያስተማርንባቸው፣ ማህበሩም በእኩል ተገኝቶ ይህን ጉባኤ ያደረገባቸው በጐጃም፣ በጐንደር፣ በትግራይ ብዙ ገዳማት አሉ፡፡ በአለም ዙሪያም በኢየሩሣሌም፣ በአሜሪካና በብዙ ቦታዎች ላይ ማህበሩ ታላላቅ ጉባኤዎች አድርጓል፡፡ ቅዱስ ኤልያስ መውረዱ ከታወጀበት ጊዜ ወዲህ ማለት ነው፡፡ ይህቺ አራት ኪሎ የምትገኘው እግዚአብሔር የመረጣትና “የቤተልሄም ዋሻ” ተብላ በተሰየመች ቦታ ላይ ነው እስከዛሬ ስንሰባሰብ የነበረው፡፡

ወደ ጥያቄው ስንሄድ ቅዱስ ኤልያስ ማን ነው?

የት ነው ያለው ቢባል ቅዱስ ኤልያስ ማለት ከዛሬ ሶስት ሺህ አመት በፊት እግዚአብሔር ያስነሳው ለእግዚአብሔር አምልኮት ቀናኢ የሆነ ልዩ ክብር የተሰጠው፣ እግዚአብሔር በእሣት ሠረገላ ያሣረገውና በመጨረሻ ዘመን መጥተህ ይሄንን አለም ትፋረዳለህ ብሎ ቃል ኪዳን የሰጠው ነው። እና ጊዜው ደቂቃው የተቆጠረለት ሱባኤ ስለደረሰ በተነገረለት ቀነ ቀጠሮ መሠረት፣ እግዚአብሔር አምላክ በሙሉ ስልጣንና ሃይል ወደዚህ ምድር ልኮታል፡፡ የቅዱስ ኤልያስ መገለጫው ትክክለኛ ቀናኢ የሆነ አምልኮተ እግዚአብሔር ይስፈን የሚለው ነው፡፡ ይሄንን ነው የሚፈልገው፤ በዚህ ይታወቃል፡፡ ሌላ ደግሞ ክፉ ስራ ሲሰራ ዝም ብሎ የሚያይ አይደለም፤ ስልጣንና ሃይል ተሰጥቶታል። ሁለተኛ አስፈሪው ነገር ይሄ ነው፡፡ ተፈጥሮን ማዘዝ ይችላል፡፡ ማንኛውንም ነገር ማከናወን ይችላል፡፡

በእርግጥ ኤልያስን በአካል ማየት ይቻላል? የት ነው ያለው?

አዎ! እግዚአብሔር ፈቅዶላቸው እና ልቦናቸውን ንፁህ ላደረጉ ቅዱስ ኤልያስ ሊያነጋግራቸው ይችላል። እኛ ከልብ የምንወዳቸውና እውነትን እንደሚናገሩ የምናምናቸው በረሃ ላይ ወድቀው ያሉ አባቶቻችን ናቸው ይህ ታላቅ ነቢይ ሰአቱና ደቂቃው ደርሶ ወደዚህ ምድር መምጣቱን የነገሩን፡፡ እና አባቶቻችንን አነጋግሯቸዋል፡፡ እሱ እንግዲህ ረቂቅ እና እሣታዊ ስለሆነ በመላው አለም መንቀሳቀስና ሁሉን ሃይል ማሳየት የሚችል ነው። ልቦናው ንፁህ ለሆነና እግዚአብሔር ለፈቀደለት ሰው በአካል ይታያል፤ ያነጋግራል፡፡ እግዚአብሔር ላልፈቀደለት ግን አይታይም፡፡ ከዚህ ቀደም ብዙ ኤልያስ ነን የሚሉ ግለሰቦች በተለያዩ ሃገራት ተከስተው ነበር፡፡ አሁንም እናንተ የህዝቡን በኑሮ መጨነቅ፣ የፖለቲካ አለመረጋጋቶች፤ እና የመጨረሻው ዘመን ቀርቧል የሚሉትን አመለካከቶች መነሻ አድርጋችሁ ነው ኤልያስ መጥቷል እያላችሁ የምታስተምሩት ይባላል?

እንግዲህ አሁን እኛ ቅዱስ ኤልያስ መጥቷል ስላልን አይመጣም፣ አልመጣም ስላልነውም አይቀርም፡፡ መጥቷል በማለታችን ደግሞ የምናገኘው ትርፍ የለም። አልመጣም ስላልን ደግሞ የምናስቀረው ነገር የለም፡፡ ትልቁ ቁም ነገር ቅዱስ ኤልያስ መጣ ሲባል ምን ማለት ነው የሚለውን መረዳት ነው፡፡ አሁን በቤተክርስቲያናችን ቅዱስ ሚካኤል መጣ እንላለን፡፡ ዳንኤል በአንበሣ ጉድጓድ በተጣለ ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ ከአንበሳ ጉድጓድ አድኖታል፡፡ እነ ሰልስቱ ደቂቅ፤ እሣት ውስጥ ሲጣሉ ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ ከእሣት አድኗቸዋል፡፡ የቅዱስ ኤልያስ መምጣት ግን ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ማንም ቅዱስ እኮ ከገነት ከብሔረ ህያዋን መጥቶ መሄድ ይችላል፡፡ አሁን ዋናው ጉዳይ መጥቷል አልመጣም የሚለው ክርክር አይደለም። የቅዱስ ኤልያስ መምጣት ዘመን፣ ሰአትና ደቂቃ ሲጠበቅለት ነበር፡፡ ያቺ ቀጠሮዋ ስትደርስ በ2000 ዓ.ም መጣ፡፡ መጣ ስንል ምን ማለት ነው፡፡ ለፍርድ ሃይል ለብሶ ስልጣኑ ተሰጥቶት አለምን ለመፋረድ መጣ ማለት ነው፡፡ አሁን በአለም ላይ ያለውን ትልቁን ስልጣን፣ በትረመንግስቱን ቅዱስ ኤልያስ ጨብጦታል፡፡ አለም በፍርድ ላይ ነው ያለችው፡፡ ማስጠንቀቂያ እየተሰጠ ነው፡፡ ትክክለኛውን መንገድ ተከተሉ፣ ሰንበትን አክብሩ፣ እውነተኛውን መስመር ያዙ እያለ ነው፡፡ ከዚህ የወጣውን ግን ይገስፀዋል፡፡ አሁን የኛ ጥረትና አባቶቻችን ያስረዱን ቅዱስ ኤልያስ የሚፈልገው ምንድን ነው የሚለውን ነው። ቅዱስ ኤልያስ ስልጣን አይፈልግም፣ የማንንም ሃብት ንብረት አይፈልግም፣ የሚፈልገው ትክክለኛ አምልኮተ እግዚአብሔር በአለም ላይ እንዲሰፍን ነው፡፡ አለም እሺ በጄ ብሎ ቢቀበል ያን ጊዜ በአክአብ ዘመን እንደነበረው በአለም ላይ ሠላም ይሰፍናል፣ በአንዲት ቅጽበት እግዚአብሔር ታላቅ ተአምራትን ያደርጋል፡፡ ስለዚህ እኛ አለም ሁሉ እንዲሰማው የሰው ልጆች እንዲገነዘቡት የምንፈልገው፣ ቅዱስ ኤልያስ በትልቅ ሃይልና ስልጣን መምጣቱን ነው፣ ማንም ከፍርዱ ሊያመልጥ አይችልም፡፡ አልመጣም ብንለውም መጥቷል ብንለውም እኛ የምንቀይረው ነገር የለም፡፡ እሱ ስልጣኑ ተሰጥቶት መጥቷል፡፡ ስለዚህ እያንዳንዱ መስመር ይያዝ፡፡ ሰንበትን ያክብር፣ እውነተኛ ተዋህዶን፣ ወልደአብ ወልደ አምላክ በተዋህዶ ከበረ፣ አንድ አምላክ አንድ ባህሪ የምትለዋን እውነተኛ አምልኮተ እግዚአብሔር የሚፈፀምባትን ተከተሉ ጠብቁ እያለ ድምፁን እያሰማ ነው፡፡ አለም ይህን እሺ ብሎ ቢቀበል ከማንኛውም ጭንቀት ሊተርፍ እና ሊድን ይችላል፡፡ ይሄን እምቢ ካለ ግን ከፍርድ ሊያመልጥ አይችልም፡፡ ሌላው መታወቅ ያለበት ቅዱስ ኤልያስ ረዳት አይሻም፤ ለምሣሌ አንድ የፖለቲካ ቡድን ቢቋቋም ገንዘብ አዋጡልኝ ይላል ወይ የሰው ሃይል ስጡኝ ይላል፣ ቅዱስ ኤልያስ ግን ይሄን አይፈልግም፡፡ ተዋህዶ ብቻ ነው የምንከተለው፣ ኦርቶዶክስ የሚለውን አንቀበልም ትላላችሁ፡፡

ምንድን ነው ልዩነቱ?

አሁን ቤተክርስትያኗ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ አይደለም እንዴ የምትባለው?

ለምንድን ነው ተዋህዶን ብቻ መነጠል ያስፈለጋችሁ?

ቅባት፣ ፀጋ፣ ሶስት ልደት እየተባለ በቤተክርስቲያናችን ውስጥ ከፍተኛ ችግር አለ። ነገር ግን ትልቁ ቁምነገር ከመጀመሪያው አንስቶ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛዋን ሃይማኖት ካስተማረ በኋላ መናፍቃን ሲነሱ፣ እነ አርዮስ፣ መቅዶንዮስ፣ እነ ንስጥሮስ ሲነሱ፣ አባቶቻችን ጉባኤ ሠርተው እውነተኛዋ ንጽህት የሆነች ተዋህዶን አንድ አካል አንድ ባህሪ ወይም በሊቃውንት አባባል “ወልደ አምላክ ወልደ ማርያም በተዋህዶ ከበረ” የምትለዋን ሃይማኖት መስክረውልናል፤ ደንግገውልናል፡፡ ይህቺን እውነተኛ መስመር ተከትለን እንድንሄድ፣ የሰው ልጅ ድህነት አግኝቶ የዘላለም ህይወት ውስጥ የሚገባው፤ ወደ ዘለለማዊ ህይወት በር የሚሻገረው፣ በዚህች እውነተኛ ጠባብ መስመር ሲጓዝ ነው፡፡ ስለዚህ የተለያዩ ኑፋቄዎች በዙሪያችን ቢኖሩም ከነዚህ ሁሉ ተጠብቀን እውነተኛ መስመር እንድንጓዝ ነው የሚፈለገው፡፡ ነገር ግን አሁን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ተብሎ እዚያ ውስጥ ብዙ ኑፋቄ፣ የለየለት ክህደት እንዳለ፣ ውስጥ ለውስጥ ብዙ ክፉ ስራ እንደሚሰራ ሁሉም የሚያውቀውና የሚገነዘበው ነው፡፡ ቀናኢ ነብይ የሆነው ቅዱስ ኤልያስ ከዚህ ሁሉ እንክርዳድ ራሳችንን እንድንጠብቅ፤ እውነተኛ መስመር እንድንከተል ነው ያዘዘን፡፡ ይህ አቋማችሁ ቤተክርስቲያኗን አይከፋፍልም? የእናንተን አካሄድ ኑፋቄ ነው በሚል የሚነቅፉ የሃይማኖቱ መሪዎች አሉ?

ማለት … የቅዱስ ኤልያስን መውረድ ነው ኑፋቄ ነው የሚሉት?

የቅዱስ ኤልያስን መውረድም ሆነ አጠቃላይ የእናንተን አካሄድ ….

አዎ እንግዲህ እሱ አለ፡፡ የተለያየ ነገር እንደሚባል ሰምተናልም አይተናልም፡፡ ነገር ግን ቀደም ብዬ እንዳስረዳሁት ነው፡፡ ይሄ እውነታ ነው፤ እኛ ስለተናገርነው የምንጨምረው ነገር የለም፤ ስላልተናገርን ደግሞ የምንቀንሰው ነገር የለም፡፡ ማንም ሊሸፍነው የማይችለው እውነት ነው፡፡ እግዚአብሔር ፍቃዱ ሆኖ አንድ ጊዜ ቅዱስ ኤልያስ ወርዷል፡፡ አሁን ይህንን ማንም ሊሰውረው አይችልም፤ እኛም ተባብረን እንሰውረው ብንል አንችልም እና ይሄን አስተውሎ እውነቱን መከተል ነው እንጂ ኑፋቄ ነው እያሉ ምክንያት መደርደር ዋጋ የለውም፡፡ ጌታ ሰው በሆነ ጊዜ በዚህ ምድር ላይ ሲመላለስ ምን ነበረ ፀሐፍት ፈሪሳውያን ያሉት፤ “ይሄ ሰውዬ የናዝሬት ሰው ነው፤ ትንቢቱ የተነገረው ከይሁዳ ወገን ነው፣ ከዳዊት ወገን በይሁዳ ይወለዳል ነው የሚለው፤ እሱ ከናዝሬት የመጣ ነው አባቱም ዮሴፍ ነው እናውቀዋለን። ይሄ ሃሰተኛ ነው” ብለው የተቻላቸውን ያህል ተቃውሞ አንስተዋል፡፡ ሆኖም የጌታን ሰው መሆን ሚስጥር ሊሰውሩት አልቻሉም፡፡ እውነትን ወደ ሃሰት ሊቀይሩት አልቻሉም፡፡ አሁንም ኤልያስ መጥቷል፡፡ ኤልያስ የሚመጣው ከኢየሩሣሌም ነው፤ የሚመጣው ከአውሬው ጋር ነው፤ በዚህ ጊዜ ነው ምናምን የሚሉ ብዙ ምክንያቶች ይደረደራሉ፤ ግን ዋጋ የለውም፡፡ እግዚአብሔር በሚስጥር ስራውን አከናውኗል፡፡ ስለዚህ ፀሐፍት ፈሪሣውያን፣ ጌታን ተቃውመው እውነትን መሰወር እንዳልቻሉት፣ አሁንም ብዙ የቤተክርስቲያን ሰዎች ቢናገሩ፣ መጽሐፍት ቢጠቅሱ፣ ይሄንን ሃቅ ሊሰውሩት አይችሉም፡፡ አንዴ እውነቱ ወጥቷል። ትልቁ ቁም ነገር የሰው ልጅ ቆም ብሎ የቅዱስ ኤልያስን መልዕክት አስተውሎ መጓዙ ላይ ነው፤ እንጂ ሃሰተኛ ነው፤ ኑፋቄ ነው፤ ቤተክርስቲያንን ይከፋፍላል ቢባል እውነቱን መሰወር አይቻልም። ልክ ያን ጊዜ ፀሐፍት ፈሪሣውያን ሆነው እንደተገኙት ነው የሚሆነው እንጂ ሌላ ትርጉም አይኖረውም፡፡

ይህ አቋማችሁ ከማህበረ ቤተክርስቲያን ያገለናል የሚል ስጋት የላችሁም?

ቅዱስ ሲኖዶስስ ሊያወግዛችሁ አይችልም?

ይህ እንግዲህ እስከ ቅዱስ ሲኖዶስ ደርሶ የመወገዝ ነገር እስካሁን የለም፡፡ በቅርቡ ግን መምህር ምህረተአብ አሰፋ ባወጡት ቪሲዲ፤ በተለይ ከየካቲት 28 ጉባኤ በኋላ፣ የጐሉ ተቃውሞዎችን አይተናል፡፡ እኛ ይሄንን መልዕክት መስጠት የጀመርነው ግን ጳጉሜ 1 ቀን 2003 ዓ.ም ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ፤ ለአባቶች፣ ለሲኖዶስ አባላት፣ ለተለያዩ ገዳማዊ አባቶችና መምህራን ትምህርቱን ሰጥተናል፤ ከብዙዎች ጋርም ተማክረናል፤ ከብዙ ደቀመዛሙርትና መምህራን ጋርም ጉዳዩን ተወያይተንበታል። መክረንበታልም። “ማህበረ ስላሴ” በተለያዩ ገዳማትና አድባራት ይህን ጉባኤ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ አሁን እንግዲህ ለሁለት አመት ያህል መሆኑ ነው። እርግጥ ያን ጊዜ ተቃውሞ የለም ማለት አይደለም፤ ሃሰተኛ ነው የሚሉም ነበሩ፡፡ እርግጠኝነቱን ተቀብሎ ዳግም ራሱን ከ“ማህበረስላሴ ዘደቂቅ ኤሊያስ” ጋር አሠልፎ የሚጓዝም አለ፡፡ ግን በሲኖዶስ ደረጃ ነገሩ የታየ አይመስለንም፤ የኛ ምኞት ግን እንዲታይ ነው። እውነቱ እንዲገለፅ ነው፡፡ ለምሣሌ አሁን መምህር ምህረተ አብ የሠጡት ምላሽ፣ የቤተክርስቲያን መልስ አሠጣጥ አይደለም፡፡ የቤተክርስቲያን መልስ አሠጣጥ ከታሪኩ እንደምንረዳው እነ አርዮስም ሲወገዙ ጉባኤ ፊት ይቀርባሉ፤ ሙሉ ሃሣባችሁን ግለፁ ይባላሉ። ለተነሣው ሃሣብ መልስ የሚሠጠው ሙሉ ጥያቄና መልስ ከተካሄደ በኋላ ነው፡፡ ይሄ ስህተት ነው፤ ይሄ እውነት ነው፤ የሚለው ፍርድ የሚሠጠው ከዚያ በኋላ እንጂ አንድ ቃል ቀንጭቦ ማጋጋል አይደለም፤ ይሄ አይነት አካሄድ የአባቶቻችን ይትበሃል እና መስመር አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ፈቃዱ ቢሆን ጳጳሣቱም ሆኑ የቤተክርስቲያን ሃላፊዎቹ አንድ ጉባኤ ሠርተው

“እስቲ ኤልያስ ይመጣል ተብሏል፤ ትንቢቱ እንዲህ ተነግሯል ጊዜው ነው?

መጥቷል ወይንስ አልመጣም?

እስቲ ምንድን ነው ምልክቶቹ?”

ሃሠት እና እውነቱ ሁሉ ለአለም ቢገለፅ የእኛም ምኞት ነው። ብዙዎቹ አሁን ይሄ ሲነገር አዕምሮአቸው የሚሄደው የስልጣን ሽሚያ፣ የሃብት ንጥቂያ ነገሮች ጋ ነው። እውነቱን ለመናገር ይሄን መልዕክት ለኛ እየነገሩን ያሉ አባቶቻችን በባዶ እግራቸው የሚሄዱ፣ እህል የማይቀምሡ፣ ራሣቸውን አሣልፈው ለእግዚአብሔር የሠጡ፣ የዚህን አለም ተድላ የናቁ ናቸው፡፡ ስለዚህ እነሡ መጥተው በጵጵስና በወርቅ ዙፋን ላይ ተቀምጠው የመኖር ሃሣብ የላቸውም፡፡ ሃሣባቸው የእግዚአብሔር አምልኮት በትክክል እንዲፈፀም ብቻ ነው፡፡ ብዙውን ጊዜ የምትሠባሠቡት ከቤተክርስቲያን ውጪ በአዳራሾች ነው፡፡ ይህ ደግሞ በቤተክርስቲያን ተቀባይነት እንደሌለው ሊቃውንቱ ያስረዳሉ፡፡ ይህንንም ኑፋቄ ነው ብለው ይነቅፋሉ … እኛ ከቤተክርስቲያን አንድም ቀን ወጥተን አናውቅም። ይሄ እምነታችን ነው፤ እውነተኛም ነው፡፡ ምናልባት ቦታው የካቲት 28 ቀን 2005 ዓ.ም እንዳደረግነው በአዳራሽ ሊሆን ይችላል፡፡ በቤተክርስቲያን ውስጥ ሲባል ሚስጥሩ ሲመረመር ትርጓሜው ቤተክርስቲያን ማለት መንፈስ ቅዱስ የሠፈረበት፣ የደናግል መነኮሣት፣ የሠማዕታት የሃዋሪያት ማህበር ያለበት፣ የእነሡ አስተምህሮ የሚነገርበት፣ እነሡ በመንፈስም በአካልም ተገኝተው የሚባርኩት ጉባኤ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ እኛ ጉባኤያችንን ለእግዚአብሄር አምልኮት ቀናኢ ሆነን እመቤታችንን ቅድስት ድንግል ማርያምን ቅዱስ ኤልያስን ይዘን ጉባኤ እስካደረግን ድረስ እኛ ያለነው በእርግጥም በቤተክርስቲያን ውስጥ ነው፤ ቁም ነገሩ ቦታውና ህንፃው አይደለም።

በቤተክርስቲያን ውስጥ ነው ጉባኤያችንን በሙሉ ያደረግነው፤ በአካል ግን በቤተክርስቲያን ውስጥ ለምን አልተደረገም ለሚለው አስቀድሜ መልሻለሁ፡፡ በተለያዩ ገዳማትና አድባራት እንዲሁም በተለያዩ ቦታዎች እየተዟዟርን በምናስተምርበት ጊዜ ቅዳሴው፣ ካህናቱ አሉ፣ ማህሌቱ በተቆመበት ነው ይህ ጉባኤ የሚካሄደው። የቅዱስ ኤልያስ መውረድም የተነገረን እንደዚሁ ነው። እኛ አሁንም ቢሆን በቤተክርስቲያን ውስጥ ነን፡፡ ትሁታን ሆነው ለገዳማት ለቤተክርስቲያናት የተለያዩ እርዳታዎችን የሚያደርጉት ደግሞ በቤተክርስቲያን ውስጥ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እየደገፉ ናቸው፡፡ ስለዚህ ከቤተክርስቲያን ተገልሎና ወጥቶ የራሱን ቡድን አቋቁሞ የሚሄድ ሠው የለም፡፡ ይህ እንደ ፖለቲካዊ ድርጅት የአመፃ አካሄድ አይደለም፡፡ እኛ በእውነተኛ ቤተክርስቲያን ውስጥ ሆነን ክፉ ነገር ከቤተክርስቲያን ይራቅ ነው የምንለው። እኛ በቤተክርስቲያን ውስጥ መሆናችንን ነው የምናውቀው። ለጊዜው በዚያች ቤት መሠባሠባችንም ሁኔታዎች ስላላተመቻቹ ነው እንጂ እኛ ቤተክርስቲያን መሄድ ጠልተን አይደለም፤ እዚያ የተለያየ ችግር አለ፡፡ እምቢተኝነት አለ፤ ሠአቱም አመቺ አይደለም፤ ማታ ማታ ስለምንሠባሠብ ያለ ሠአት ለምን ትገባላችሁ ትወጣላችሁ ማለት ይመጣል፡፡ ይሄ ሁሉ ችግር ስላለ ነው፡፡ ባጭሩ እኛ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዳለን ነው የምናውቀው፤ አባቶቻችን ከእኛ ጋር ናቸው፡፡ በብዙ ገዳማት አባቶች አሉን፣ ባህታውያን አሉን፣ በጳጳሣት ደረጃም ብዙዎች አሉን፡፡ እኔ ስማቸውን አልጠቅስም ግን ልቦናቸው ከዚህ ጋር የሆነ አብረውን በዚህ እውነት የሚጓዙ በአለም ዙሪያ ብዙ የእግዚአብሔር ወዳጆች አሉ። ከዚህም በላይ በአይን የማይታዩ ቅዱሣን ሁሉ ከእኛ ጋር መሆናቸውን በእርግጠኝነት እናምናለን አምነናልም፡፡

እርስዎ እንደሚሉት ሳይሆን የራሣቸውን ሃይማኖት ፈጥረዋል ነው የምትባሉት?

ከመካከላችሁ “እኔ ኤልያስ ነኝ” የሚል እንዳለም ይነገራል?

ለዚህ እንግዲህ የማቀርበው መልስ መድሃኒታችን ኢየሡስ ክርስቶስ በመጣ ሠአት ከህገ ኦሪት ወደ ህገ ወንጌል አሸጋግሮናል፡፡ ያን ጊዜ መድሃኒታችን ኢየሡስ ክርስቶስ አዲስ ሃይማኖት መስርቷል? ይሄን ነው ለነዚህ ወገኖች እንደ ጥያቄ የምናቀርበው፡፡ ከህገ ኦሪት ወደ ወንጌል ሲሸጋገር አዲስ ሃይማኖት አልመሠረተም። ሃይማኖት አንዲት ነች ለመላዕክት የተሠጠች፣ በህገ ልቦና የነበረች በህገ ኦሪት የተነገረች፣ በህገ ወንጌል የተመሠረተች፣ አለምን አሣልፋ የምትኖር አንዲት ሃይማኖት ነች፡፡ ስለዚህ አሁንም ለዘመናት ትንቢት ሲነገርለት የነበረ ነብይ ነበረ፡፡ ሠአቱ ደቂቃው ደርሶ እሡ ሲመጣ በቤተክርስቲያን ውስጥ ለዘመናት ተሸሽገው ሲሠሩ የነበሩ አጓጉል ነገሮች ነበሩ፡፡ ይሄ በተንኮል ነው የተሠራው፤ መስመሩን እንዲህ አድርጋችሁ አስተካክሉ፣ ቀጥተኛ የቀድሞውን መስመር ተከተሉ ብሎ መስመሩን ቅዱስ ኤልያስ አሣይቶናል፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ኤልያስ የሚፈልገው የቀደመችውን መስመር አጥርተን እንድንሄድ እንጂ አዲስ ሃይማኖትን አይደለም፡፡ ልክ ጌታ፤ ህገ ኦሪት ላይ ተመስርቶ ህገ ወንጌልን ብሩህ አድርጐ እንዳሣየ፣ ኤልያስም ለዘመናት ሲሠሩ የነበሩ ተንኮሎችና አጓጉል መስመሮችን አጥርቶ ትክክለኛውን መስመር እንድናይ አደረገ እንጂ አዲስ ሃይማኖት አይደለም የፈጠረው፡፡ ሃይማኖት አንዲት ናት እሷም ተዋህዶ፡፡ ኤልያስ ወረደ ማለት አዲስ ሃይማኖት አይደለም፡፡

ይልቅስ እነሡ ይወርዳል የሚል መፅሃፍ ነው የያዙት ማድረግ ያለባቸው እንዴትና መቼ የሚለውን በሚገባ መመርመር ነው። በአጭሩ እኛ የመሠረትነው አዲስ ሃይማኖት የለም። በማህበራችን ውስጥም እኔ ኤልያስ ነኝ ያለ አንድም የለም፡፡ ኤልያስ በመላው አለም ቦታና ስፍራ ሣይወስነው በእሣት ሠረገላ ያለ ነው፡፡ ሠንበት ቅዳሜ እንጂ እሁድ አይደለም ትላላችሁ? ይህን ለማለት መነሻችሁ ምንድን ነው? በእርግጥ ሠንበት አንዲት ናት እሷም ቅዳሜ ነች። ይህ እንግዲህ ቅዱስ ኤልያስ ተሠውረው የነበሩ እውነቶችን ሲገልጥ ከተገለጡት አንዱ ነው። ቅዳሜ እና እሁድ ሁለቱም ሠንበት እንዴት ሊባል ቻለ? የሚለውን ከታሪክ መዛግብት በሠፊው ማወቅና መገንዘብ ይቻላል፡፡ ከ4ኛው መቶ አመት ጀምሮ ነው ለ1600 አመታት እሁድ ሠንበት ሲባል የኖረው በተንኮል የገባ ነው፡፡ እግዚአብሔር ስድስት ቀን ፈጥሮ ሠባተኛ ቀን ላይ ያረፈባት ሠንበት ተብላ የተጠራችው ቅዳሜ ነች፡፡ እሁድ እሁድ ነው የራሱ ስም አለው፡፡ እሁድ ብሎ ጀምሮ ቅዳሜ ላይ ያበቃል። በኢትዮጵያም ከታሪክ እንደምንረዳው ሁለት ታላላቅ ጉባኤዎች ተደርገው ሠንበት የትኛው ነው የሚል ጥያቄ ተነስቶ ነበር። ነገስታቱ ማስታረቅ ስላቃታቸው እሁድ ሠንበት ይባል ማለታቸውን ታሪክ ያስረዳናል፡፡ እሁድ የጌታ ትንሣኤ ነው፤ የፅንሠት ቀንም ነው፤ ስለዚህ እሁድን በእሁድነቱ እናከብረዋለን፡፡

አርማችሁ ላይ የዳዊት ኮከብንና የ“ቶ” ምልክትን ነው የምትጠቀሙት ይህ ከአይሁድ እምነት ጋር አይቆራኝም?

እንግዲህ እግዚአብሔር አምላክ ለቅዱሣን ሁሉ ታላላቅ ምልክቶችን ሠጥቷቸዋል፡፡ በእርግጥ እስራኤል ይሄንን የዳዊት ኮከብ የሚባለውንና አሁን በቤተ መንግስታቸው ዙሪያ ያለውን ምልክት ይዘውታል፡፡ በሠንደቅ አላማቸው ላይም ይጠቀማሉ፡፡ ነገር ግን ኮከቡ ራሱን የቻለ ታላቅ ሚስጥር ያለው ነው፤ የመንፈስ ቅዱስ ሃይል ያለው ምልክት ነው፡፡ የስድስቱን ቀን ስነ ፍጥረት ስድስት ጫፎቹ ያስረዳሉ፤ መሃሉ ደግሞ ሠንበትን የሚያመለክት ነው፡፡ “ቶ” ሠባተኛዋ ፊደል ነች፡፡ ሠባት ቁጥር ትልቅ ትርጉም ያላት ነች ፍፁምነትን የምታመለክት ነች፡፡ ሠባተኛው ዙፋን የጌታ እንደሆነ፣ ሠባተኛው ቀን ሠንበት እንደሆነች፣ 7 ቁጥር ብዙ ሚስጥር አላት፡፡ “ቶ” ሠባተኛዋ ቁጥር በመሆኗ ፍፁምነትን የምታመለክት ነች፡፡ ክርስቶስን የምትወክል ነች፡፡ ክርስቶስ ለኛ ሲል በቀራኒዮ መስቀል ላይ ራቁቱን መሠቀሉን የምታመለክት ነች። ትልቁ ከዚህ በላይ ያለው ሚስጥር አባቶቻችን ከቅዱስ ኤልያስ የተረዱት ያን ጊዜ በመላዕክት አለም ውጊያ ተደርጐ ነበር፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ቅዱስ ገብርኤል ከሣጥናኤል ጋር ሲዋጉ ሁለት ጊዜ ተሸንፈዋል፡፡ በሶስተኛው እንዲያሸንፉ ሲልካቸው ይህን ቀስተደመና ቀርፆ፣ ይህን ምልክት የኮከቡን ቅርፅ የ“ቶ” ቅርፅ ያለው መስቀል በየክንፋቸው ቀርፆላቸዋል፡፡ አንዱ የሠጣቸው ትልቅ ሃይል ኮከቡ እና “ቶ” የሚለው ቅርፅ ነው፡፡ ስለዚህ ይህን ተዘንግቶ የነበረውን ቅዱስ ኤልያስ የኛ መሆኑን አውቀን እንድናነሣው አድርጐናል፡፡ ለክርስቲያኖች በሙሉ ዲያብሎስን ድል እንድንነሣበት የተሠጠን ነው እንጂ እንደተባለው ክርስቶስን ከሠቀሉት ጋር የማበርና በእነሡ መስመር የመጓዝ ነገር አይደለም። ነጭ ልብስ ነው መለበስ ያለበት የሚል አዋጅም አውጃችኋል? ይህ ነጭ ልብስና ቀስተ ደመና ያለበት ልብስ ሃይል ነው፡፡ ጥቁር ልብስን በተመለከተ ጥቁር ልብስ አጉል ነገር ነው፡፡ ተንኮል አለበት፡፡ በግብፅ አባቶቻችን ክርስቲያኖች ይኖሩ በነበረ ሠአት በሙስሊሞች ተፅዕኖ ነው ጥቁር ልብስ እንዲለበስ የተደረገው፡፡ ቅዱስ ኤልያስ በዘመናት የተሠራውን ተንኮል ስለሚያውቅ የክርስቲያኖች ልብሳቸው ነጭ መሆን እንዳለበት አውጇል፡፡ ይህም የተሠጣቸውን ተስፋ እና ትንሣኤ የሚያመለክት ነው። ስለዚህ ነው ጥቁር ልብስ ይቅር የሚል ታላቅ አዋጅ ከቅዱስ ኤልያስ የተነገረን፡፡ በተለይ ካህናት ነጭ ወይም ሌላ አይነት ቀለም ያለው ልብስ መልበስ አለባቸው፡፡ ጥቁር ልብስ መልበስ በሠይጣን አገዛዝ ስር ያለን መሆናችንን የሚያመለክት ነው፡፡ ከጥቁር ውጪ ሌላ አይነት መልበስ ይቻላል፡፡ የአንገታችን ማህተብ እና የልብሣችን ዘርፍ የቀስተደመና ቀለም መሆኑም ሃይል ያላብሠናል፡፡

ባለፈው ሳምንት በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት አካባቢ በርካታ ወጣቶች “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚል ጥቅስ የታተመበት፤ ወይንጠጅ ቀለም ያለው ተመሳሳይ ቲሸርት ለብሰው በጋራ ሲጓዙ ትኩረቴን ሳቡት። እኔ ብቻ ሳልሆን ሌሎች መንገደኞችም በነገሩ መሳባቸው አልቀረም፡፡ አንዳንዶች እንደውም ቀረብ ብለው ሲጠይቁ ሰምቻለሁ፡፡ ለመሆኑ ቲ-ሸርቱ ላይ የሰፈረው ጥቅስ መልዕክት ምንድነው? ሃሳቡን ካመነጩት ስድስት ወጣቶች ጋር ጋዜጠኛ ብርሃኑ ሰሙ ቃለምልልስ አድርጓል፡፡ በቲ-ሸርት ላይ መልእክት ለማስተላለፍ መነሻና ምክንያት የሆናችሁ ምንድነው? የኮተቤ መምህራን ትምህርት ኮሌጅ የማታ ተማሪዎች ነን፡፡

በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ትምህርት ክፍል ለሦስት ዓመታት የተሰጠንን የአማርኛ ቋንቋ አጠናቀን የዚህ አመት ተመራቂዎች ስለሆንን ደስታችንን በምን እናድምቅው ብለን ስናስብ፣ በአማርኛ ቋንቋ ዙሪያ የሚታይ ችግርን የሚያመለክትና የሚያወያይ መልእክት ማስተላለፍ ስለፈለግን “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚል ጥቅስ በቲ-ሸርት ላይ አሳትመን በመልበስ እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ ምን ያህል ተማሪዎች ናችሁ ለዚህ ዓላማ በጋራ እየተንቀሳቀሳችሁ ያላችሁት? በእኛ ዲፓርትመንት በማታው ክፍለ ጊዜ የምንማር ተማሪዎች ብዛት 116 ስንሆን በሦስት የተለያዩ ክፍሎች ነው የምንማረው፡፡ በምረቃችን ዋዜማ በጥቅስ መልእክት የማስተላለፉ ሀሳብ የመነጨው በአንደኛው ክፍል በምንገኝ ስድስት ጓደኛሞች ቢሆንም አሁን ሁሉም የማታው ክፍለ ጊዜ ተመራቂ ተማሪዎች ደግፈውት በጋራ እየተንቀሳቀስን ነው፡፡ አማርኛ ቋንቋ ላይ ተጋርጧል የምትሉት ችግር ምንድነው? ቋንቋው ላይ ችግር ተከስቷል ብለን ግንዛቤ ለማስጨበጥ በጋራ እየተንቀሳቀስን ካለነው ተመራቂ ተማሪዎች መሀል አንዳንዶቻችን በግልም፣ በመንግሥትም ትምህርት ቤቶች ስለምናስተምር በተግባር ብዙ ችግር በየእለቱ እናያለን፡፡

ተማሪዎች በትምህርት ቤት ግቢ ወስጥ አማርኛ ቋንቋ እንዳይናገሩ የሚከለክሉ ትምህርት ቤቶች አሉ፡፡ በአማርኛ ቋንቋ የሚናገር ተማሪ ሀፍረት እንዲሰማው የሚያደርግ ተግባር ሲፈፀምባቸው ይታያል፡፡ አማርኛ ቋንቋ ከትምህርት ቤቱ ግቢ በ200 ሜትር ርቀት ብቻ ነው መናገር የሚቻለው የሚል ሕግ ያወጡ ትምህርት ቤቶችም አሉ፡፡ ወላጆች የትኛው ትምህርት ቤት ነው እንግሊዝኛ ጥሩ የሚያስተምረው እያሉ ነው ልጆቻቸውን ወደ ትምህርት ቤት የሚያስገቡት፡፡ ይህ ልማድ በጊዜ ካልተቀጨ በጥቂት አመታት ውስጥ ወጣቶች ለማንነት ቀውስ ችግር መጋለጣቸው አይቀርም፡፡ ይህ አደጋ መነጋገሪያ እንዲሆን በመሻት ነው እኛም ጥቅሱን አሳትመን በመልበስ በመንቀሳቀስ ላይ ያለነው፡፡ ቋንቋው በንግግር ብቻ ሳይሆን ለፅሁፍም ከማገልገሉ ጋር በተያያዘ ተከስቷል የምትሉት ችግር አለ? አማርኛ፤ እንግሊዝኛ ቋንቋ እያሳደረበት ባለው ጫና ምክንያት ለችግር መጋለጡን ለሕብረተሰቡ እያመለከቱ ያሉ ሌሎች አካላትም አሉ፡፡ በኢትዮጵያ የመገናኛ ብዙሃን የቋንቋ አጠቃቀም ዙሪያ በጌታቸው በልዩ የተሰራ ጥናት አለ፡፡

ከሌሎች የአገራችን ቋንቋዎች በተሻለ ሁኔታም በአማርኛ ቋንቋ ዙሪያ ብዙ ጥናት ተሰርቷል፡፡ እንዲህም ሆኖ የአውሮፓውያን አስተሳሰብ በተለያየ መልኩ ጫና እያሳደረብን እንዳለው ሁሉ፣ ቋንቋችን ዋነኛው ሰለባ እየሆነ መምጣቱ በትምህርት ቤቶች ብቻ ሳይሆን በተለያዩ እለታዊ እንቅስቃሴዎቻችን ውስጥ ይታያል፡፡ “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚለው መልእክታችን አማርኛ ቋንቋን ማዕከል ያደረገ ቢሆንም ሌሎች የአገራችን ቋንቋዎችንም ይመለከታል፡፡ ቋንቋ መግባቢያ ብቻ ሳይሆን ባህል፣ እምነት፣ ወግ፣ ልማድ፣ መከባበር፣ መተሳሰብ፣ ሀዘን ደስታ… መግለጫ ነው፡፡ የራስን ቋንቋ እንደሚገባው አለማወቅ ለማንነት ቀውስ ችግር ይዳርጋል የምንለው ለዚህ ነው፡፡ አማርኛ የፌደራሉ መንግሥት የሥራ ቋንቋ ነው፡፡ በአገራችን ልጆች አፋቸውን በፈቱበት ቋንቋ እንዲማሩ ተወስኗል፡፡ በአዲስ አበባ የሚወለድ ልጅ አፉን የሚፈታው በአማርኛ ቢሆንም በትምህርት ቤቶች ግን በእንግሊዝኛ ቋንቋ የላቀ ችሎታ እንዲኖረው እየተሰራ ወይም የወላጆች ፍላጐት እንደዚያ እንዲሆን የመፈለግ አዝማሚያ በስፋት ይታያል፡፡ ይህ ጅማሬ በዚሁ መልኩ እያደገ ከሄደ በማንነታችን ላይ ጉዳት ማስከተሉ አይቀርም፡፡

በየእለቱ ቅላፄያቸው ወደ እንግሊዝኛ ቋንቋ የተለወጡ የአማርኛ ቃላትን እንሰማለን፡፡ በሙዚቃችን ውስጥ እንዲህ አይነቱ ነገር እየበዛ መጥቷል፡፡ የተማሩ የሚባሉ ሰዎች ብቻ ሳይሆኑ ፊደል ያልቆጠሩ እናቶቻችንም በንግግሮቻቸው መሀል ብዙ የእንግሊዝኛ ቃላት ሲጠቀሙ እየሰማን ነው፡፡ ቋንቋ የሚፈጠረውና የሚያድገው አንዱ ከሌላው እየወሰደና እየሰጠ ስለሆነ እንዲህ መሆኑ ምን ይገርማል? ችግሩ መቀባበሉ ላይ ሳይሆን አወሳሰዱ ላይ ነው፡፡ ሁሉም ቋንቋ ሀሳብን ለመግለፅ በራሱ ምሉዕ ነው ተብሎ ይታመናል፡፡ አማርኛ ቋንቋ በአባባል፣ በተረት፣ በእንቆቅልሽ፣ በሥነቃል የዳበረና ሀሳብን ለመግለፅ ምንም ችግር የሌለበት ሆኖ ሳለ፣ በንግግር መሐል እንግሊዝኛ ቃላትን መጠቀም አዋቂና የተማረ ያሰኛል ስለሚባል፤ ፋይዳቸው ምንም የሆነ የእንግሊዝኛ ቃላት በአማርኛ መሀል መጨመር ተለምዷል፡፡ ለምሳሌ ተማሪዎቻችንን ለፈተና እየተዘጋጃችሁ ነው? ብለን ስንጠይቃቸው “ዌል ዝግጁ ነን” የሚል መልስ ይሰጡናል፡፡ በዚህ መልስ ውስጥ “ዌል” የሚለው የእንግሊዝኛ ቃል መጨመሩ ያስገኘው ምንም ጥቅም የለም፡፡ በአማርኛ ቋንቋ ውስጥ ከሌሎች ቋንቋዎች ወስደን የምንገለገልባቸው ብዙ ቃላት አሉ፡፡ ቴሌቪዥንና ሬዲዮ የሚሉትን ቃላት እንደምሳሌ መጥቀስ እንችላለን፡፡

የቴክኖሎጂ ስያሜዎች ወደ አገራችን ሲገቡ በአገራችን አባባል የሚተረጉም አካል አለመኖሩ ለችግሩ የራሱ የሆነ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ለምሳሌ ጀርመኖች የቴክኖሎጂ ቃላትን በራሳቸው አባባል ተርጉመው የቋንቋቸው አካል ያደርጋሉ፡፡ በእኛ አገር ሲሆን የሚታየው ግን ከዚህ በተቃራኒ ነው፡፡ ከቴክኖሎጂ ማደግ ጋር የሚፈጠሩ ስያሜዎች በየእለቱ ወደ ቋንቋዎቻችን ይገባሉ። ከዚህም ባሻገር ከበድ ያሉ ፅንሰ ሀሳቦችን ተጨማሪ ማብራሪያ ለማያስፈልጋቸው አባባልና አገላለፆች ሁሉ የእንግሊዝኛ ቃላትን መጠቀም እየበዛ መጥቷል፡፡ የተቀላቀለ ቋንቋ የሚናገር ሰው በበዛ ቁጥር ቅይጥ ማንነት ያላቸው ሰዎች ይበረክታሉ፡፡ የአማርኛ ቋንቋም የመጥፋት አደጋ እንደተጋረጠበት ይነገራል፡፡ በእኛም አገር “እንግአማ” ላይ ይወድቃል፡፡ ሂንዱ የሚባለው የሕንዶች ቋንቋ በእንግሊዝኛ ተፅእኖ ስር ወድቆ የመጥፋት አደጋ እየተፈጠረ ስለሆነ “ሳይቃጠል በቅጠል” እንደሚባለው መፍጠን ይኖርብናል፡፡ “እንግአማ” ምንድነው? እንግሊዝኛና አማርኛ ከሚሉት ሁለት ቃላት ተውጣጥቶ የተገኘ ቃል ሲሆን በሁለቱ ቃላት የተመሰረተ አዲስ ቋንቋ ለማለት ነው፡፡ አንድ ሰው ሁለት ማንነት ሊኖረው አይችልም፡፡ “እንግአማ” ሁለት ማንነት ይፈጥራል፡፡ አማርኛ ቋንቋ በዘይቤ የወሎ፣ የጐንደር፣ የጐጃም፣ የሰሜን እና የሸዋ በሚል በአምስት የተለያዩ ክፍሎች ይመደባል፡፡ የገጠር አማርኛ ተናጋሪዎች ሁሉ የእንግሊዝኛ ቃላትን እየደረቱ ሲጠቀሙ መስማት ተለምዷል፡፡ ቋንቋችን ጉራማይሌ ከሆነ ማንነታችንም ጉራማይሌ ይሆናል። አንድ የሬዲዮ ጋዜጠኛ “Part of the body” የሚለውን የእንግሊዝኛ ሐረግ ተናግሮ አብሮት ለሚወያየው የሥራ ባልደረባው “በአማርኛ ምንድነው የሚባለው?” ብሎ ትርጉም ሲጠይቀው ሰምተናል፡፡

ችግሩ እስከዚህ ድረስ ሰፍቶ የሚታይ ነው፡፡ እኛ እንግሊዝኛ ቋንቋን እያጥላላን አይደለም። እንግሊዝኛን ማወቅ የለብንም አላልንም። እንግሊዝኛን ብቻ ሳይሆን ሌሎች የአገርና የዓለም ቋንቋዎችንም ማወቅ ብንችል አንጐዳም፡፡ ማንነታችን ላይ ቆመን ሌላውን ለማወቅ ካልጣርን ግን ጉራማይሌ ማንነት ነው የሚኖረን፡፡ በአገር ውስጥ በሌሎች ቋንቋዎች ጫና ምክንያት ጉዳት ሲደርስበት የሚከላከልለት የሌለ የሚመስለው አማርኛ ቋንቋ፤ አሜሪካንን በመሳሰሉ ኢትዮጵያዊያን በብዛት በሚኖሩባቸው አገራት እንግሊዝኛን አሸንፎ ለመነጋገሪያነት መዋሉን እንሰማለን፡፡ ቻይናም በአገሯ በዩኒቨርስቲ ደረጃ ዜጐቿ እንዲማሩ እያደረገች ነው፡፡ ሌሎች ይህን ያህል ዋጋ ከሰጡት እኛ ከነሱ በላይ ልናከብረውና ልንጠነቀቅለት ይገባል፡፡ የአማርኛ ቋንቋ ትምህርት በአገር ውስጥ በተለያዩ የትምህርት ተቋማት ይሰጣል፡፡ የተለያዩ መፃህፍትም ይታተማሉ፡፡ ቋንቋውን ለመጠበቅና ለማዳን በተለይ ሕብረተሰቡን ማዕከል ያደረገ ሰፊ ሥራ መሰራት ይኖርበታል፡፡ ለዓላማችሁ ድጋፉን የሰጠ ማን አለ? ተቃውሞስ አልገጠማችሁም? ያለውን አደጋ መከላከል የሚያስችል ግንዛቤ ለማስጨበጥ ስንነሳ መምህር ደብሬ “ጉራማይሌ ቋንቋ፣ ጉራማይሌ ማንነት ይሆናል” የሚለውን ጥቅስ በመስጠት ተባብራናለች፡፡

መምህር የሻው ተሰማን መሰል መምህራንም ጥሩ ነው በማለት አበረታተውናል፡፡ ጥቅስ የታተመበትን ቲ-ሸርት ለብሰን በየአደባባዩ ስንንቀሳቀስ የሚያዩን ሰዎች ዓላማችንን እየጠየቁን ስንነግራቸው እንድንበረታና ሀሳቡን ለሚመለከታቸው አካላት እንድናደርስ በርቱ ይሉናል፡፡ ተቃውሞ ግን እስካሁን አልገጠመንም፡፡ ተመርቃችሁ ከወጣችሁ በኋላስ ለዚህ ዓላማችሁ ለመንቀሳቀስ ምን እድልና ተስፋ አላችሁ? አብዛኞቻችን አስተማሪ ስለምንሆን በተማሪዎቻችንና በትምህርት ቤታችን አካባቢ የምንሰራው ነገር ይኖራል፡፡ ስብስባችንም ሳይበታተን ለዚሁ ዓላማ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር የእግር ጉዞን መሰል የቅስቀሳ መድረኮች የማሰናዳትም እቅድ አለን። የምረቃችንን ዋዜማ በጭፈራና ሆይ ሆይታ ሳይሆን እንዲህ ባለ ቁምነገር ላይ ማሳለፋችንም እያስደሰተን ነው፡፡

“ዓለምን የቸገራት ምንድን ነው? ምግብ? ልብስ? ቤት? አዎን፤ በሙሉም ባይሆን በከፊል የነዚህ ነገሮች ችግር አለባት፡፡ …ነገር ግን እስካሁን ድረስ መድኃኒት ያልተገኘለት ችግር የመልካም ሰዎች ማነስ ነው” ይላል አቤ መስከረም 10 ቀን 1957 ዓ.ም ለ4ኛ ጊዜ ባሳተመውና “ምልከዓም ሰይፈ ነበልባል” የሚል ርዕስ በሰጠው መጽሐፉ፡፡ ምልክዓም ሰይፈ ነበልባል ከ”አልወለድም” እና “አንድ ለእናቱ” ቀጥሎ ብዙ አንባቢ ያገኘ መጽሐፍ መሆኑን አዲስ ዘመን ጋዜጣ በወቅቱ መዘገቡን አንብቤያለሁ፡፡ ምልክዓም ሰይፈ ነበልባል የመጽሐፉ ርዕስ ብቻ ሳይሆን ዋና ወኪል ባለታሪክም (ገፀ ባህርይ የሚባለው) ነው፡፡ አቤ፤ ሰዎች መብታቸውን ማስከበር ያለባቸው ከተወለዱና ካደጉ በኋላ ብቻ ሳይሆን ገና በእናታቸው ማህፀን ሳሉ…“እውነት በሌለበት ዓለም ለመኖር አልወለድም” ብለው እንዲሟገቱ የጻፈና በዚህም፤ መጽሐፉ ለእሳት፣ እሱ ደግሞ ለቁም እስር፣ ለግዞትና ለእንግልት የተዳረገ ጽኑዕ ደራሲ ነበር፡፡ “አልወለድም” የሚል ተዓምረኛ ፅንስ ፈጥሮ እንዳሳየን ሁሉ “ምልክዓም” የተባለ ሰው “ቤትኤሌፋኦስ” ብሎ በጠራት ሀገር ፈጥሮና በፕሮቴስታንት ሚሲዮን ስርዓት አሳድጐ ለጠቅላይ ሚኒስትርነት ማዕረግ ያበቃዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራትን አገር ህዝብ ሁሉ ስለሚወድና እንደቤተሰቡ ስለሚያምን በሚወዳቸው ሰዎች አማካይነት የተመረዘ ምግብ ይበላና ይሞታል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሊሞት ሲያጣጥር በኑዛዜ መልክ የተናገረውንና በህይወት እያለ “ለፓርላማ እያቀረበ ያስፀደቃቸው ናቸው” ብሎ ነው አቤ ዝርዝር ዕቅዶችንና የተደረጉ ክርክሮችን በዝርዝር ያሳየን፡፡ መጽሐፉ የሚጀምረው ከጠቅላይ ሚኒስትሩ የ”ውጭ ነፍስ፣ ግቢ ነፍስ” ጣር ላይ ነው፡፡ ከዚያም በህይወት ታሪክ መልክ መልእክቱን ያስተላልፍልናል። ምልክዓም ያገሩን ህዝብ በእጅጉ የሚወድና “ፈጣን ለውጥ” ማምጣት የሚፈልግ፣ በርካታ የለውጥ እርምጃዎችን ወስዶም በአገሩ ህዝብ ዘንድ ተወድዶ የሚከበር ጠቅላይ ሚኒስትር ነበር፡፡ “እኛ ከታላቅ ግብ የምንደርሰው በነፃነትና በኅብረት በምንሠራው ጠንካራ ሥራ ብቻ እንጂ የአንዳንድ መንግሥታት ጥሩንባዎች ሆነን በምናገኘው ምጽዋት አይደለም፡፡ እኛ ነፃ ሕዝብ ነን፡፡

የሚወዱንን የማንወድበት፣ የሚጫኑንን የማንቃወምበት ምክንያት የለንም” ይላል ምልክዓም የውጭ ፖሊሲውን አስመልክቶ፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም “ዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም ዕርዳታና ብድር እንድንፈቅድላችሁ ዝለሉ ሊል ይችላል፡፡ ቶሎ ብለው “ስንት ጊዜ እንዝለል?” የሚል ጥያቄ የሚያቀርቡ መንግሥታት ይኖራሉ፡፡ አኛ ግን ቢያንስ “ለምን? ብለን እንጠይቃለን፡፡” ሲሉ አድምጠናቸዋል፡፡ ምልክዓም በሀገረ ቤትኤልፋኦስ ውስጥ “ፈጣን ለውጥ” ለማምጣት ሌት ከቀን ይሰራ ነበር፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም “ፈጣን ለውጥ” የሚሉትን ቃላት እንደ ዳዊት ከመደጋገም አልፈው በተግባር ለመተርጐም ደፋ ቀና ሲሉ ሞት ቀደማቸው፡፡ “ግማሾች ወገኖቼ በቁንጣን፤ ግማሾቹ በረሃብ ሲሞቱ ለማየት አልሻም፡፡ በሚገባ ሁኔታ ማደላደል፤ ቁንጣንንም ረሃብንም ማጥፋት ስለሚቻል ሁሉንም በሚገባ ለማደላደል ዝግጁ ነኝ” ይላል የአቤው ጠቅላይ ሚኒስትር ምልክዓም፡፡ በሶሻሊዝም ደቀመዝሙርነታቸው የሚታወቁት ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም፤ በአገሪቱ ውስጥ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል እንዲኖር ተግተው እንደሚሰሩ፤ በተለይ አዲስ አበባን አሁን ካለችበት ሶስት ደረጃ ወደ ሁለት ለማጠጋጋት እንደሚጥሩ ሲገልጹ ነበር፡፡ ንግግራቸውን በተግባር ለመግለጥም የጋራ መኖሪያ ህንፃዎች በብዛት እንዲሰሩ ፓርቲያቸው ዕቅድ ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ነበር፤ ነውም፡፡

የምልክዓምን ዋና ዋና ተግባራት በተመለከተ ደራሲው (አቤ ጉበኛ) እንዲህ ይገልፀዋል፡፡ “አምስት ዋና ዋና ግድቦች” አሰርቶ የኤሌክትሪክ ቢያዎች በብዛት እንዲቋቋሙና የመስኖ ልማት በጣም እንዲስፋፋ አደረገ፡፡ አርባ ታላላቅ ፋብሪካዎች፣ ስምንት መቶ ቀላል ኢንዱስትሪዎች፣ 550 ታላላቅ የማህበር እርሻዎች እንዲቋቋሙ አደረገ፤ ሁለት የብረት ማቅለጫ፣ አንድ የመዳብ ማቅለጫ ጣቢያዎችንም አቋቋመ፡፡ ከሶስት ቦታዎች ላይ የነዳጅ ዘይት ፍለጋ ሥራ እንዲጀመር አድርጐ ፍለጋው ታላቅ ተስፋ ባለው ሁኔታ ይጣደፍ ነበር” ኢህአዴግም ከዚህ በላይ የተጠቀሱትንና “ምልክዓም አከናወናቸው” የተባሉትን ተግባራት የመሰሉ የኃይል ማመንጫ፣ ፋብሪካ፣ የመስኖ ግድብና የነዳጅ ዘይት ፍለጋ ተግባራትን ትኩረት ሰጥቶ እያከናወነ ይገኛል፡፡ “ትምህርት ቤቶች በሁለት ዕጥፍ እንዲጨምሩ አደረገ፡፡ የሃገሩ አውራጃዎች በባቡር እንዲገናኙ ከማድረጉ በላይ በአንዳንድ ቀበሌዎችም የባቡር ሃዲድ መዘርጋት እንዲጀመር አስደርጓል” (ገፅ 27) በዘመነ ኢህአዴግም ትምህርት ቤቶች በእያንዳንዱ ቀበሌ ገበሬ ማህበር ከመሰራታቸው በተጨማሪ የዩኒቨርሲቲዎች ቁጥር ከሁለት ወደ ሰላሳ አንድ እንዲያሻቅብ አድርጓል፡፡ የባቡር መስመሩም እንደ አቤ ጉበኛው ምልክዓም ተጠናቅቆ ስራ ላይ ባናየውም ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት፤ እንዲያውም በአምስት ዓመቱ የለውጥና የተሃድሶ ዕቅድ ዘመን ውስጥ አምስት ሺህ ኪሎሜትር ሃዲድ ለመዘርጋት አቅዶ እየሰራ ነው፡፡ ግን ከሥራ ዘመኑ ላይ አቤ እና ኢህአዴግ የሚለዩበት መስመር አለ፡፡ የአቤው ምልክዓም ያንን ሁሉ ተግባር ያከናወነው በስልጣን ላይ በቆየባቸው 13 ዓመታት ሲሆን ኢህአዴግ ሊገነባ ያሰበው በአምስት ዓመታት ብቻ ነው፡፡

እርግጥ ኢህአዴግ 11 የሥልጣን ዘመናቱን የፈጀው በስብሰባና አገርን በማረጋጋት ላይ ነው (ከ1983-1994)፤ ከ1995 ዓ.ም በኋላ በተለይም ከ1997 ዓ.ምህረቱ የምርጫ ውጤት ጋር ተያይዞ ከእንቅልፉ ሊባንንና የሚታይ የልማት ውጤት ለማስመዝገብ ችሏል፡፡ “ህዝብ ወዶ ሲጠላኝ ከማየት አለመኖሬን እመርጣለሁ፡፡ …ተወዶ እንደመጠላት ተከብሮ በገዛ ተግባር እንደመናቅ ያለ የሞት ሞት ወዴት አለ” የሚለው ምልክዓም ፤ በራስ ጥረት ማደግ እንደሚቻል ጠንካራ እምነት ነበረው፡፡ መራሔ ኢህአዴጉ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም፤ ዘላቂ ልማት የሚመጣው በሃገሬው ህዝብ ጠንካራ ጥረትና የተባበረ ትግል እንጂ በውጭ መንግሥታት ዕርዳታና ብድር አለመሆኑን ይናገሩ ነበር፡፡ ለማስረጃም ታላቁን የህዳሴ ግድብ በእኛው መዋጮና አቅም ለመገንባት መሠረቱን ጥለዋል፡፡ “አንድ አገር የተፈጥሮ ሃብቶቹን ለተወላጆቹ በበቂ ሊሰጥ ካልቻለ አገርነቱ ብቻ ሊያኮራ አይችልም። ለተራበና የዕለት ፍላጐቶቹን ካላገኘ ሰው ሀገርና ነፃነት ከሚለው ቃል ይልቅ ምግብና ልብስ የሚለው ቃል ይሰማዋል” ይላል ምልክዓም የሀገርን ትርጉምና የህዝብን ሀገራዊ ቁርኝት ሲገልጽ፡፡ ምልክዓም አስተዳደርን አስመልክቶም “ማንም ህዝብ ሥነ ሥርዓት ያለው አስተዳደር፣ ትክክለኛ ፍርድና ፀጥታ ያለው ኑሮ ከነፃነት ጋር ካላገኘ ምንም ነገር ሊሠራ አይችልም” የሚል አቋም ነበረው፡፡ ኢህአዴግም ምንም እንኳን ሃሳቡን በገቢር መግለጽ አቅቶት እየተንገዳገደ ቢገኝም “መልካም አስተዳደር የልማት መሠረት ነው” ብሎ እንደሚያምን ደጋግሞ ሲናገር ይደመጣል፡፡

እንዲያውም ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ጉቦኞችንና ለመልካም አስተዳደር ጠንቅ የሆኑትን ሰላቢዎች በሁለት በመክፈል “የመንግስትና የግል ሌቦች” ብለው መናገራቸው አይዘነጋም፡፡ ምልክዓም ዳቦንና ኑክሊዬርን በማነፃፀርም እንዲህ ብሎ ነበር “ያገራችን ህዝብ ሁሉ በቀላሉ ሊሠራቸው የሚችላቸውን ሥራዎች በተፋጠነና ጠቃሚ በሆነ መንገድ በመሥራት እንድንበለጽግ ነው፡፡ ከአቶሚክ ቦንብ ይልቅ ዳቦ ብዙ ፈላጊ አለው። ግዴላችሁም ሞኝ አንሁን፡፡ በዓለም ውስጥ በብዙ ሚሊዮን የሚቆጠሩ ሕዝቦች በረሃብ የሚሰቃዩት ምግብ ስላነሰ እንጂ የኒክሊዬር ቦምብ ስለጠፋ አይደለም” ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም የኢትዮጵያ ሕዝብ ቀንደኛ ጠላት ድህነት መሆኑን፣ ይህንን መሠረታዊ ጠላት ለማሸነፍም ከትጥቅ ትግሉ በላይ መራራ ትግል እንደሚጠይቅ ደጋግመው ይናገሩ ነበር፡፡ “የሀገራችንን ሕዝብ ሠርቶ እንዳይጠቀም እያሰናከልን ‘አገራችን ለውጭ አገር ዜጐች ክፍት ናት፡፡ እንግዳ ተቀባዮች ነን፡፡ ብዙ የውጭ አገር ዜጐች በሀገራችን ውስጥ በደስታ ይኖራሉ’ በሚሉ የራስ ማታለያ ቃሎች ራሳችንን እየሸንገልን በሀገራችን ያሉትን ጠቃሚ ጠቃሚ የሥራ ቦታዎች ለውጭ ዜጐች ብንሰጥ ሕዝቡ አውቆ ሊቃወመን ባይችል እንኳ እግዚአብሔር ይፈርድብናል” ይል ነበር ምልክዓም፡፡ ይህን ድርጊትም ኢህአዴግ እየፈፀመው ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም በየክልሉ ለውጭ ዜጐች ዓይናቸው ያየውንና ልባቸው የከጀለውን ያህል መሬት እየሰጠ፤ ዜጐቹን ግን “ደን ጨፍጭፈዋል” በሚል የዋህ ሰበብ ከደቡብ፣ ከኦሮሚያ እና ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በጠራራ ፀሐይ ሲያፈናቅልና ሲያባርር ተስተውሏል፡፡

አረብና ፓኪስታን መጥቶ በግሬደር ድራሽ አባቱን የሚያጠፋው ዛፍ ግን የኢትዮጵያ ሃብት አይደለም፡፡ ወይም ጥፋት የሚሆነው በኢትዮጵያውያን መጥረቢያ ሲቆረጥ ብቻ ነው፡፡ “አገራችንን ማልማት የሁላችንም ተግባር ስለሆነ ለዚህ ተግባር ከየግል ጥቅማችን በከፊል ለጥቂት ጊዜ መስዋዕት ማድረግ ግዳጃችን ነው፡፡ ብዙ ደሞዝ ያለን ከደሞዛችን እየቀነስን ለልማት ባጀታችን ማሙያ የገቢ ምንጭ መፍጠር አለብን፡፡ …40 ሚሊዮን የሆንን ያገራችን ሰዎች በዓመት አንዳንድ ብር ብናወጣ 40 ሚሊዮን ብር እናገኛለን፡፡ በዚህ በአንድ ዓመት በሚገኘው ብቻ ብዙ ክሊኒኮች፣ ብዙ ትምህርት ቤቶችና አንዳንድ መንገዶች መሥራት እንችላለን” (ገፅ 49፣ 50፣ 100-101) ኢህአዴግም ለሚያከናውነው የልማት ተግባር የአርሶ አደሩ ጉልበትና የከተማ ነዋሪው መዋጮ ከፍተኛ ዋጋ አላቸው ብሎ ያምናል፤ አምኖም ተግባራዊ እያደረገው ነው፡፡ የአቤ ጉበኛው ምልክዓም ስንፍናንም ይኮንን ነበር “የማይሠሩት የሚሠሩትን የሚንቁበትና የሚያጠቁበት ጊዜ አልፏል፡፡ ሠራተኞቻችን ትሁት የሆነ ንቃት መንቃት አለባቸው፡፡ ጨዋ የሆነ ደስታ መደሰትም ይገባቸዋል፡፡” (ገፅ 77) የሥራን ክቡርነት፣ የተመጻዳቂነትን መርዘኛነት ደርግ ገላልጦ ቢያሳይም ኢህአዴግ በተግባር አውሎታል፡፡ ዛሬ በየሰፈሩ ተደራጅተው ደረቅ ቆሻሻ የሚያነሱ፣ በጥርብ ድንጋይ ንጣፍ ህይወታቸውን የሚመሩ በርካታ ወጣቶችን ማየት የተለመደ ሆኗል።

ህዝቡ ቀልጣፋ አገልግሎት የሚያገኝበትን መንገድም ምልክዓም ተልሞ ነበር፡፡ “አንድ ባለጉዳይ ለማንኛውም የመንግሥት መ/ቤት ጉዳዩን ሲያመለክት በጠየቀበት ቀን መልስ ማግኘት አለበት” የሚሉና ሌሎች መሠረታዊ የአሠራር መመሪያዎችን ከማውጣቱም በላይ ለተግባራዊነቱ የቅጣት ህጐችንም አውጥቷል፡፡ ኢህአዴግም ምንም እንኳ በጽናት ባይቀጥልበትና የራሱን ሌቦች መቆጣጠር ባይችልም መሠረታዊ የአሠራር ለውጥ (ቢ.ፒ.አር) አካሂዶ በአንዳንድ መ/ቤቶች፣ ለምሳሌ ውልና ማስረጃና ኢሚግሬሽንና የዜግነት ጉዳይ ተቋማት የሚያስመሰግን ውጤት አሳይተው ነበር፡፡ ክትትል ባለመኖሩ ግን ወደነበሩበት ጐታታ አሠራር ተመልሰዋል፡፡ “…የግል ጠላቱን በመንግሥቱ ክብር ህግ ተጠግቶ የሚያጠቃ አገረ ገዥ፣ ዳኛ፣ ፖሊስ ወዮለት! ለሕዝብ አገልግሎት፤ ወንጀልን ለማስወገድና የሕዝብን መብትና ፀጥታ ለማስከበር ተመርጦ ራሱ የወንጀል መሪ የሆነ ባለሥልጣን ወዮለት” ሲል ምልክዓም ወስላታ ባለስልጣናቱን ያስጠነቅቅ ነበር፡፡ ኢህአዴግም ጠንከር ያለ እርምጃ መውሰድ አልቻለም እንጂ በጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካይነት “የእኛ ሌቦች” እያለ ባለሥልጣናቱን ሲወርፍ ይደመጥ ነበር፡፡ “ኪራይ ሰብሳቢ” የሚል የበረሃ ስምም አውጥቶላቸዋል፡፡ “የሰይጣን ሕግ ከእግዚአብሔር ሕግ ጋር ተስማምቶ ሰውን የሚጠቅም ሆኖ ባገኘው በርሱ ከመጠቀም አልመለስም” ይላል የአቤው ምልክዓም። ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም “ከበጣም መጥፎ መጥፎ፤ ይሻላል” የሚል ፈሊጥ ነበራቸው፡፡ “ሹመት የጡረታ አበል ወይም የማባበያ ጉቦ አይደለም” የሚል አቋም ያለው ምልክዓም “በመልካም አገር ተፈጥሮ መደህየት፣ የወንጀልና የሥራ ፈትነት ብዛት፤ የሰነፍ መሪዎችና ፈራጆች የሥራ ውጤቶች ናቸው” ይላል፡፡

እንደ ሃሳባቸው ስሉጥ የሥራ መሪዎችን (ባለሥልጣናትን) ማግኘት አልቻሉም እንጂ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስም አደገኛ ቦዘኔነትን ለማጥፋትና አምራች ኃይሉን ለማብዛት ጥረት ያደርጉ ነበር፡፡ በጣም የገረመኝ ጉዳይ ደግሞ የመኖሪያ ቤት ዕጥረትን ለማቃለል ምልክዓምም የተጠቀመበት ዘዴ ነው፡፡ “…1ኛ” የመንግስት ሠራተኞች ለግል ባለጥቅሞች ገባር በመሆን የኑሮ ቀንበር እንዳይከብዳቸው በማንኛውም መንገድ የኑሮአቸውን ሸክም ማቃለል አለብን፡፡ ሀ) የመንግሥት ሠራተኞች መኖሪያ ቤቶች መሥሪያ የ30 ሚሊዮን ብር በጀት ለመጀመሪያ ጊዜ መንግሥታችን መድቧል፡፡ ለ) በከተማዎቻችን ውስጥ ቤቶች እየተሰሩ ለመንግሥት ሠራተኞች ይሰጣሉ፡፡ የመንግሥት ሠራተኞችም ለቤቶቹ የሚወጣው ገንዘብ ከደሞዛቸው እየተቀነሰ እስኪመለስ ድረስ ይከፍላሉ። ሐ) ያከፋፈሉም ሁኔታ፤ ለግል ባለቤቶች መቶ ብር ኪራይ ይከፍል የነበረው ሐምሳ፤ ሐምሳ ይከፍል የነበረው ሃያ አምስት፤ በጠቅላላው ማንም ሰው ድሮ ይከፍል የነበረውን ግማሽ እየከፈለ መንግሥት ለሠራለት ቤት ያወጣውን ገንዘብ ይመልሳል፡፡ መ) ዕዳውን በረጅም ጊዜ ከፍሎ ከጨረሰ በኋላ ቤቱና ቦታው የራሱ ንብረት ሆኖ ይፀናለታል፡፡ 2ኛ. መንግሥት በአንድ በኩል ገንዘብ ሲያወጣ ባንድ በኩል ደግሞ ሠራተኞች ከሚኖሩባቸው ቤቶች የሚያገኘው ተመላሽ ገቢ ባጀቱን ሳያቋርጥ እንዲቀጥል ስለሚያደርግለት፤ ይህ ዓይነቱ ሥራ ሳያቋርጥ መቀጠል አለበት” (ገጽ 95-96) ኢህአዴግም የተጠቃሚውን ስብጥር አሰፋው እንጂ፤ በገቢር እየተረጐመው ያለው ይህንኑ የምልክዓምን ዕቅድ ነው ማለት ያስችላል፡፡ “እሱን አይደለም” ቢባል እንኳ “ተመሳሳይ ነው” ብሎ መከራከር ይቻል ይመስለኛል፡፡

ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ በስፋት እየተገነቡ የሚገኙ የጋራ መኖሪያ ህንጻዎችና የ40/60 ፕሮጀክቶች ለዚህ አሳማኝ ዋቢዎች ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ የመሬት ባለቤትነትን በተመለከተም ምልክዓም የሚከተለውን አቅዶ ነበር “…የአንዳንድ ሰዎችን ቁጣ እየፈራን የሃገራችንን ጠቅላላ ጥቅም የሚጐዳ ነገርን ዝም ብለን ማየት የለብንም፡፡ 1ኛ) ለርሻ የሚሆኑ መሬቶች ሁሉ ለሀገራችን ገበሬዎች ይደለደላሉ፡፡ የጢሰኛና ገባር ታሪክም በዚህ ያበቃል፡፡ 2ኛ) በታወቀ ጊዜ በገንዘብ ሳይገዛ በልዩ ልዩ የማጭበርበር ምክንያት ብዙ የከተማ ቦታ የያዘ ከሁለት ቤቶች በላይ ያለው ሰው በቦዘን ያስቀመጠው ቦታ ቢገኝ፤ መንግሥት የቤት መሥሪያ ገንዘብ እያለው መሬት ለሌለው ሰው ይሰጣል፡፡ 3ኛ) ማንኛውም ሰው መንግሥት ሳያውቅ መሬት መግዛት፣ ሻጩም መሸጥ አይፈቀድለትም” (ገፅ 97) ሰው ከእንስሳት በታች ይታይ በነበረበት ዘመን ላይ አቤ ይህን ደፍሮ መጻፉ ያስደንቃል፡፡ ምንም እንኳ የጢሰኛና ገባርን ሥርዓት በማፈራረስ መሬትን ለአራሹ ያደረገው ደርግ ቢሆንም ኢህአዴግም ይህንኑ ሥርዓት ጠንክሮ ቀጥሎበታል፡፡ የህገወጦች የመሬት ወረራ ከቁጥጥሩ በላይ ስለሆነበትም ነባር ይዞታዎችን ሁሉ ወደ ሊዝ የሚያስገባ አዋጅ ለማውጣትም ተገዷል፡፡ “እኛ የሕዝብ ባለዕዳዎች ነን እንጂ ሕዝብ የኛ ባለዕዳ አይደለም፡፡ የተማርነውም የተሾምነውም በህዝብ ላይ ስለሆነ የሕዝብ አሸከርነታችንንና ባለዕዳ መሆናችንን ማመን አለብን” ይላል ምልክዓም፡፡ ኢህአዴግም መሠረታዊ የአሰራር ለውጥ (ቢ.ፒ.አር) እና የማህበራዊ አገልግሎት መልሶ ማዋቀር (ሲቪል ሰርቪስ ሪፎርም) ለማምጣት ደፋ ቀና ሲል ነበር፡፡ ግን ሁሉም ተጨናግፎበታል፡፡

  • ከቤተክርስቲያን ጋር ፀብ የለንም፤ ለአመፃ አልመጣንም” (“የማህበረ ዘደቂቅ ኤሊያስ” መሪዎች)
  • “በማህራችን እኔ ኤልያስ ነኝ የሚል አላጋጠመኝም”
  • “ነብዩ ኤልያስ በነገረን መንገድ የጥንቷን ሃይማኖት እያስተካከልን ነው -
  • “ቅዱስ ኤልያስ በኢትዮጵያ ሚሊኒየም ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየተዘዋወረ ነው”

ነብዩ ኤልያስ ለፍርድ ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየታየ ነው ከሚለው እምነታቸው ጋር በተያያዘ ድንጋይ ተወርውሮባቸው በተፈጠረ ሁካታ ለሰባት ቀናት ታስረው የነበሩት አባ ዮሴፍ ብርሃነ፣ አርቲስት ጀማነሽ ሰለሞን፣ መምህር ወልደመስቀል ፍቅረማሪያም እንዲሁም ፕሮፌሰር ይስማማው አለሙ፤ ሃይማኖታችን ተዋህዶ ነው፤ ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል አላግባብ የተጨመረ ነው ይላሉ፡፡ “ማህበረ ዘደቂቀ ኤልያስ” በሚል ስያሜ ራሳቸውን የሚጠሩት የማህበሩ መሪዎች፤ አዲስ ሃይማኖት እንዳልፈጠሩ ሲያስረዱ፣ የጥንቷን እውነተኛ ሃይማኖት ወደ ትክክለኛ ቦታዋ እንድትመለስ እያደረግን ነው ብለዋል፡፡ ይህን የምንሰራው ነብዩ ኤልያስ በነገረን መንገድ እንጂ እኛ በመሰለን መንገድ አይደለም የሚሉት የማህበሩ መሪዎች፤ በማህበሩ ውስጥ ኤልያስ ነኝ የሚል ሰው የለም ብለዋል፡፡

ከማህበሩ መሪዎች መካከል አንዱ የሆኑት አባ ዮሴፍ ብርሃነ “ኤልያስ ወደ ምድር መጥቷል” በሚለው እምነታቸው ዙሪያ ተጠይቀው፤ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ አለምን ለመፋረድ ከገነት ወደ ምድር ወርዶ በእሳት ሰረገላ እየተዘዋወረ ነው ብለዋል፡፡ ኤልያስ መጥቷል ስላልን አይመጣም፡፡ እኛ ኤልያስ አልመጣም ስላልን አይቀርም ያሉት አባ ዮሴፍ፤ ኤልያስ እንደሚመጣ በመፅሃፍ ቅዱስ በግልፅ የተነገረ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን የሚመጣበት ጊዜም ስለተጠቀሰ ጊዜውን አስልቶ ማወቅ ይቻላል ብለዋል፡፡ ከአንዳንድ ሰዎች ዘንድ ተቃውሞ እንደተሰነዘረባቸው ያመኑት አባ ዮሴፍ፤ እስካሁን ጉዳዩ በሲኖዶስ ቀርቦ እንዳልተወገዘና ሲኖዶሱ ጉዳዩን ቢመረምረው እንደሚወዱ ገልፀዋል። ማህበሩን ከተቀላቀለች አንድ አመት ከ7ወር እንደሆናት የገለፀችው አርቲስት ጀማነሽ፤ አንዳንድ ሰዎች ጀማነሽ የመሠረተችው አዲስ ሃይማኖት መጥቷል በሚል ህብረተሰቡን እያደናገሩ ነው ካለች በኋላ፣ እኔ የመሠረትኩት አዲስ ሃይማኖት የለም ብላለች፡፡ “ተዋህዶ” የሚለው ስም ከጥንት የኖረ የሃይማኖታችን መገለጫ እንጂ እኔ የፈጠርኩት አይደለም ያለችው አርቲስቷ፤ “እውነትን እየተናገረ በሚኖር ሰው ላይ ክፉ ስም እየለጠፉ ለማሳደድና እውነትን ለመደበቅ ከመሞከር እውነቱን መመርመር ይሻላል” ብላለች፡፡

ኦርቶዶክስ የሚለው ቃል አላግባብ የተጨመረ መሆኑን የሚያምኑት የማህበሩ መሪዎች፤ የጥንቷ እውነተኛ ሃይማኖት መገለጫዋ ተዋህዶ የሚለው ስያሜ ነው ብለዋል፡፡ “ኤልያስ መጥቷል ትላላችሁ፤ ኤልያስ በማህበራችሁ ውስጥ አለ ወይ?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ፤ “ኤልያስ መጥቷል አልመጣም የሚለው መልዕክት ሊያከራክር ቢችልም፣ እስካሁን በማህበራችን እኔ ኤልያስ ነኝ የሚል አላጋጠመኝም” ብላለች፡፡ መ/ር ወልደመስቀልም በበኩላቸው፤ በበረሃ ያሉ፤ በፆምና በፀሎት የተጉ አባቶቻችን ኤልያስ ተገልጦላቸዋል፣ ዳሷቸዋል፣ አነጋግሯቸዋል” ብለዋል፡፡ በፖሊስ የታሰሩበትን ምክንያት ተጠይቀው ሲመልሱ፣ በሚያዝያ 16 ቀን የኪዳነምህረትን ዝክር ለመዘከር 4 ኪሎ ቅድስት ስላሴ ቤተክርስቲያን አካባቢ ወደ ምትገኝ የማህበሩ መሰብሰቢያ ቤት ፀበል ፃዲቅ ይዘው በሚሄዱ አባላት ላይ አንዳንድ የሠፈሩ ወጣቶች ድንጋይ በመወርወራቸው በተፈጠረ አለመግባባት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በወጣቶቹ ድርጊት አንዲት ታዳጊ መፈንከቷን የገለፁት የማህበሩ መሪዎች፤ በእለቱ በከሣሽነት ወደ ፖሊስ ጣቢያ ሄደው የከሳሽነት ፎርም ሞልተው ቃላቸውን ከሰጡ በኋላ፣ በጣቢያው አዛዥ ውሳኔ የከሳሽነት ቃላቸው ተቀይሮ በተከሳሽነት ቃላቸውን እንዲሰጡ መደረጋቸውን ተናግረዋል፡፡

ከከሳሽነት ወደተከሳሽነት እንዲቀየሩ የተደረገው ቀደም ሲል የአካባቢው ሰው ለፖሊስ ጣቢያው ተደጋጋሚ አቤቱታ በማቅረቡ መሆኑን መምህር ወልደመስቀል ተናግረዋል፡፡ ማህበሩ መርሃ ግብሮችን ሲያከናውን ድምጽ ይረብሸናል የሚሉ አቤቱታዎች እንደቀረቡብን ተረድተናል፣ ነገር ግን በፍርድ ቤት ሲቀርቡ በደፈናው ሁከት ፈጠራችሁ የሚል ክስ ነው የተመሰረተብን ብለዋል የማህበሩ መሪዎች፡፡ በመጀመሪያ የፍርድ ቤት ውሎ የዋስ መብታቸውን ቢጠይቁም፤ መርማሪው የአካባቢው ህብረተሰብ ቦታውን ለቀው እንዲወጡ የሚል አቤቱታ እያቀረበ ስለሆነ ጉዳዩ እስኪጣራ የዋስ መብታቸውን እቃወማለሁ በማለቱ ለ7 ቀናት በእስር መቆየታቸውን የገለፁት የማህበሩ መሪዎች፤ በመጨረሻ ግን ስትፈለጉ ትቀርባላችሁ ተብለው እያንዳንዳቸው በ500 ብር ዋስ እንደተለቀቁ ተናግረዋል፡፡

በአሜሪካ፣ “serial killer” ተብሎ በፖሊስ የሚታደን ሰው…

በኛ አገር “አርበኛ” ወይም “ጀግና” ተብሎ ሊወደስ ይችላል (በአብዮቱ አመታት ሲተላለቁ እንደነበሩት አብዮተኞች)

በፈረቃ ከምትሰራበት በርገር ኪንግ እንደወጣች ጠፍታ የቀረችው አማንዳ ቤሪ፣ “ፊቷን አየሁ፤ ድምጿን ሰማሁ” የሚል ሰው ሳይገኝ 11 አመታት አልፈዋል። የጠፉ ልጆችና ልጃገረዶች፣ በሁለት ቀናት ውስጥ ተፈልገው ካልተገኙ ብዙውን ጊዜ መጨረሻቸው አሳዛኝ ነው። ተገድለው ነው የሚገኙት። ሳምንት ሙሉ ተፈልጋ ያልተገኘችው አማንዳ፣ ከዚህ ዘግናኝ ህልፈት አትተርፍም የሚል ነበር የመርማሪዎች ግምት። አስገራሚው ነገር ከሳምንት በኋላ፣ ለእናቷ አንድ የስልክ ጥሪ ደረሰ። የተደወለው ከአማንዳ ሞባይል ነው። የእናቷን ድንጋጤና ጭንቀት ልክ አልነበረውም። ስልኩን ሲያነሱት ግን፣ የልጃቸውን ድምፅ አልሰሙም። ሞታለች የሚል መርዶም አይደለም። ከአማንዳ ጋር ተጋብተን ሚስቴ ሆናለች የሚል የወንድ ድምፅ ነው የሰሙት። በኢትዮጵያዊኛ ቋንቋ ብንተረጉመው፣ “ጠልፌ ወስጃታለሁ፤ ጠልፌ አግብቻታለሁ” እንደማለት ነው። በቃ፣ ስልኩ ተዘጋ።

የአማንዳ እናት መረጃውን ለፖሊስ ቢያደርሱም፣ የፖሊስ ምርመራና ፍለጋ ባይቋረጥም፣ ውጤት አልተገኘም። ከአመት በፊትም፣ ከዚያው አካባቢ አንዲት ወጣት ሴት ጠፍታለች። ከአማንዳ በኋላም እንዲሁ፣ ከተመሳሳይ ቦታ ሌላ የ14 አመት ሴት እንደወጣች ቀርታለች። የት ይግቡ፣ የት ይድረሱ ፍንጭ አልተገኘም። በእርግጥ አንዲት ጠንቋይ በቴሌቪዥን ስርጭት አማንዳ ህይወቷ አልፎ አስከሬኗ ጥልቅ ባህር ውስጥ ሰጥሟል ብላ እንደተናገረችውም አልሆነም። ሶስቱ ሴቶች ከነሕይወታቸው ከአስር አመት በላይ ሲሰቃዩ የኖሩት፣ አማንዳ ከጠፋችበት አካባቢ ብዙም የማይርቅ መኖሪያ ቤት ውስጥ ነው - በሶስት በአራት ኪሎሜትር ርቀት። በኤርየል ካስትሮ ተጠልፈው ከታገቱበት እለት ጀምሮ፣ ሶስቱ ሴቶች ከቀን ቀን፣ ከአመት አመት፣ ቤት እንደተዘጋባቸው መከራ ይበላሉ።

ለመውጣት ቢሞክሩ፣ ድብደባውና እርግጫው! አሁንም በኢትዮጵያዊኛ ቋንቋ እንግለፀው ከተባለ፣ “ከቤት ንቅንቅ ብትይ እግርሽን እሰብረዋለሁ” እያለ ሚስቱን ነጋ ጠባ የሚያሰቃይ ባል እንደማለት ነው። እንዴት ብትሉ፤ ከሁለት ሳምንት በፊት ኢቲቪ በሁለት ክፍል ካቀረበው ድራማ መልሱን ማግኘት ይቻላል። “ጠልፎ ማግባት” በህግ የተከለከለ የወንጀል ድርጊት መሆኑን ለማሳየትና፣ “ለህብረተሰቡ ግንዛቤ ለማስጨበጥ” ታስቦ የተሰራ ድራማ ነው። እንግዲህ አስቡት። “ጠልፎ ማግባት” ብዙም እንደ ወንጀል ስለማይቆጠር፣ “በሽማግሌና በእርቅ” ሊያልቅ የሚችል ቀላል ጉዳይ እንደሆነ ተደርጎ ስለሚታሰብ… ያን ያህልም “ጉድ! ጉድ! አቤት ጭካኔ!” የሚያሰኝ አይደለም ማለት ነው። እናም፤ “ጠለፋ ወንጀል ነው” እያሉ “በድራማ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ጥረት ማድረግ” አስፈለገ። ገና እዚህ ደረጃ ላይ ነን ያለነው። ከኢትዮጵያውያን መካከል ግማሾቹ፣ ባል ሚስቱን የመደብደብ መብት አለው ብለው እንደሚያምኑም ባለፉት አስር አመታት የተካሄዱ ሶስት ተከታታይ ጥናቶች ያረጋግጣሉ።

በአጭሩ፣ ጠልፎ ማግባትና ማሰቃየት፣ ብዙ ጣጣ የለውም። ድብቅነትን አይጠይቅም። በአሜሪካ ግን፣ ጣጣው ብዙ ነው። ጠልፎ ማግባት ይቅርና፣ ሚስትን “የት ወጣሽ የት ገባሽ” እያሉ ማሰቃየት እንደ ተራ ነገር አይቆጠርም። በዝምታ የሚታለፍ ቢሆን ኖሮማ፣ ኤርየል ካስትሮ ከመጀመሪያ ሚስቱ ጋር ባልተለያየ ነበር። የኤርየል ቤትና የሚስቱ ወላጆች ቤት ቅርብ ለቅርብ ቢሆንም፣ እየመጡ እንዲጠይቋት ወይም እየሄደች እንድትጠይቃቸው አይፈልግም ነበር። አንዳንዴ እሱ በማይኖርበት ሰዓት እህቷ ልትጠይቃት ስትመጣ እንኳ፣ በሩ ስለሚቆለፍ መግባት አትችልም። ኤርየል፣ ሚስቱን ቤት ውስጥ ቆልፎባት ነው የሚሄደው። ከዚያም ድብደባ ተጨመረበት። አንዴ አፍንጫዋን ሰብሯታል። ሚስቱን በመደብደቡ ሁለቴ የታሰረው ኤርየል፣ ባህሪውን ሊያሻሽል ስላልቻለ ሚስት በፍቺ ጥላው ወጣች - በፖሊስ ታጅባ። “ሚስቱን ቢደበድብ መብቱ ነው” የሚል አይነት አስተሳሰብ በስፋት የሌለበት አገር ውስጥ፣ “ውልፊት ትይና እግርሽን እሰባብረዋለሁ” እያለ እድሜ ልክ ሚስቱን እያሰቃየ መኖር አይቻልም - ማንም እንዳያውቅ ደብቆ ካላሰቃየ በቀር። ኤርየልም፣ ይህንኑን ነው ያደረገው - ጠልፎ እየወሰደ በድብቅ ማሰቃየት።

እንደ ኢትዮጵያ በመሳሰሉ አገራት፣ በሃይማኖትና በብሄረሰብ ስም፣ በአገርና በህዝብ ስም፣ ሰውን የማጥቃትና የማሰር፣ የማሰቃየትና የመግደል… ቅስቀሳዎች ወይም ዘመቻዎች በየጊዜው በግላጭ ይፈፀሙ የለ? ይህንን የሚፈፅሙ ክፉ ሰዎች፣ ለጭካኔያቸው ሰበብና ማመካኛ አያጡም። እንዲያውም፣ “አገር ወዳድ አርበኛ፣ ቆራጥ አብዮተኛ፣ የቁርጥ ቀን ጀግና”… የሚል ውዳሴ ይጎርፍላቸዋል። ስቃይና ግድያ የሚፈፅሙትም በግላጭ ነው። እንደ አሜሪካ በመሳሰሉ በስልጣኔ ደህና የተራመዱ አገራት ውስጥ ግን፣ ሰውን በግላጭ ለማሰቃየትና ለመግደል የሚያስችል ሰበብና ማመካኛ ማግኘት ከባድ ነው። ክፉ ሰዎች፣ በግላጭ እንዳሻቸው ጭካኔ እየፈፀሙ በየአደባባዩ መፈንጨት አይችሉም። በድብቅ ስቃይና ግድያ ለመፈፀም የሚሞክሩ ግን አይጠፉም - ለምሳሌ ልማደኛ ነፍሰ ገዳዮች (serial killers)። ልዩነቱን አያችሁት። በኋላ ቀር አገራት ውስጥ፣ ክፉ ሰዎች ለጭካኔያቸው ብዙ አይነት ማመካኛ ማቅረብ ስለሚችሉ፣ በአደባባይ ሰውን እያሰቃዩና እየገደሉም፣ እንደ ጀግና ወይም እንደ አርበኛ ይታያሉ። በስልጣኔ ደህና የተራመዱ አገራት ውስጥ ግን፣ ክፉ ሰዎች “ልማደኛ ነፍሰ ገዳይነታቸውን” የሚሸፋፍኑበት እድል ስለሌላቸው በፖሊስ ይታደናሉ። እንደ ኢትዮጵያ በመሳሰሉ አገራት፣ “ልማደኛ ነፍሰ ገዳዮች (serial killers) የሌሉ ይመስለናል። በሌላ ስም ስለምንጠራቸው ነው - አርበኛ፣ አብዮተኛ፣ ጀግና እየተባሉ ይጠራሉ። እንደ ኤርየል ካስትሮ፣ በድብቅ የእገታና የማሰቃየት ጭካኔ የሚፈፅሙ ሰዎች በአገራችንና በሌሎች ኋላቀር አገራት የሌሉ ከመሰለ ንም ተሞኝተናል። ሞልተዋል። ግን፣ ጭካኔያቸውን ያን ያህልም መደበቅ አያስፈልጋቸውም። ሳልፈቅድልሽ ከቤት ወጥተሻል ብሎ ሚስቱን ቢደበድብ ብዙም ችግር አይገጥመውማ።

ባለ 5 ኮከቡ ካፒታል ሆቴልና ስፓ ትናንት ተመርቆ አገልግሎት ጀመረ፡፡ በ172 ሚሊየን ብር የተሠራው ሆቴሉ 114 የመኝታ ክፍሎች አሉት፡፡ በአቶ የማነ ገ/ሥላሴ ባለቤትነት የተገነባው ይኼ የግል ሆቴል መዋኛ፣ የሴቶችና የወንዶች መታሻ ክፍሎችና መዋቢያ፣ አንድ ፎቅ ጂምናዚየም፣ ባር፣ ላውንጅ፣ የስብሰባ አዳራሾች አሉት፡፡ ግንባታው አምስት ዓመት የፈጀው ሆቴል፤ በማስፋፊያው ባለ 11 ፎቅ ሕንፃ እያስገነባ ሲሆን ከምድር በታች ሁለት ፎቅ የመኪና ማቆሚያ አለው፡፡

ሆቴሉ በአሁኑ ወቅት ለ225 ዜጐች የሥራ ዕድል የፈጠረ ሲሆን የሠራተኞቹን ቁጥር 270 የማድረስ ዕቅድ አለው፡፡ አቶ የማነ ገ/ሥላሴ የሆሲ ትሬዲንግ ሃውስ ባለቤት ሲሆኑ ድርጅታቸው አሉ ከሚባሉት የገቢና ወጪ ንግድ ድርጅቶች አንዱ ነው፡፡ ሆሲ በብረታ ብረት ማሽኖች፣ መሳሪያዎችና ሌሎች ተዛማጅ ንግዶች ላይ የተሰማራ ሲሆን፤ የእርሻ ምርት ውጤቶችንም ለውጭ ገበያዎች በማቅረብ ይታወቃል፡፡

የማተሚያ ማሽኑ ዋጋ 8ሺ ዶላር ነው፤ ስምንት ሺ ሽጉጦችን ሊሰሩበት ይችላሉ። ፅሁፍ የሚያትም ሳይሆን ሽጉጥ ወይም ሌላ እቃ የሚያትም ማሽን ነው - 3D printer ይሉታል። የዘንድሮ ምርጥ ፈጠራ እንደሆነ የተነገረለት “ቅርፅ አታሚ ማሽን”፣ በሚቀጥሉት አመታት ገበያውን እንደሚያጥለቀልቅ ተተንብዮለታል። ትንቢቱ ወር ሳይሞላው፤ አለምን ሲያነጋግር የሰነበተ የህትመት ውጤት ብቅ አለ - በማተሚያ ማሽን የተሰራ የመጀመሪያው ሽጉጥ። መልኩ ከዘመናዊ የቢሮ ፅሁፍ ማተሚያ ማሽን በመልክ ብዙም አይራራቅም። አሰራሩም ተመሳሳይ ነው - ከኮምፒዩተር በሚደርሰው ትዕዛዝ አትሞ ማውጣት (ፅሁፍ ሳይሆን ቅርፅ)። የመጀመሪያው የሽጉጥ እትም በዚሁ ሳምንት በአደባባይ ተሞክሮ የመጀመሪያውን ጥይት ተኩሷል። ዲፈንስ ዲስትሪቢዩተር በተባለ ኩባንያ ተሰርቶ የተሞከረው ሽጉጥ Liberator የሚል ስም ተሰጥቶታል - ነፃ አውጪ እንደማለት። ሽጉጡ ከፕላስቲክ የተሰራ ቢሆንም፣ ማንም አላናናቀውም - የመተኮስ ስራውን በአግባቡ የሚያውቅ ነውና። ፍርሃት ያደረባቸው ግን አሉ።

ብዙዎቹ የመፈተሻ መሳሪያዎች፣ ብረታማ ነገሮችን ለይተው እንዲያሳዩ የተሰሩ ናቸው። የፕላስቲክ ሽጉጥ የታጠቀ ሰው፣ የፍተሻ መሳሪያዎች ሳያግዱት ማለፍ የሚችል መሆኑ፣ አንዳንድ የአሜሪካ ህግ አውጪ ምክርቤት አባላትን አሳስቧል። የጦር መሳሪያ ቁጥጥር አከራካሪ በሆነበት ወቅት፣ የብዙዎችን ትኩረት የሳበ አዲስ አይነት ሽጉጥ መፈጠሩ፣ አጋጣሚውን አስገራሚ አድርጎታል። ደግሞም ማንም ሰው በየቤቱ ኮምፒዩተርና “ፕሪንተር”ን እየተጠቀመ ሊፈበርከው ይችላል። በእርግጥ “ማንም ሰው ይችላል” የሚለው አነጋገር የተጋነነ ነው። ከኮምፒዩተሩ ወደ ፕሪንተሩ የሚተላለፈውን ትዕዛዝ (ንድፍ) አስተካክሎና ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል። ይህንን ደግሞ “ማንም ሰው ይችለዋል” የሚባል አይደለም። ነገር ግን፤ ብዙዎችን አላስጨነቃቸውም።

ምክንያቱም፣ የአዲሱ ሽጉጥ ንድፍ በኢንተርኔት ተሰራጭቷል። ፎርብስ መፅሄት እንደዘገበውም በጥቂት ቀናት ውስጥ ከ100 ሺ በላይ ሰዎች፣ ንድፉን ከኢንተርኔት አግኝተው የራሳቸው አድርገውታል። ደግሞም፣ ሌሎች አማራጮች አሉ። የጦር መሳሪያ ባለቤት የመሆን መብት እንዲከበር በሕገመንግስት ባወጀችው አገር ውስጥ፣ መንግስት በጦር መሳሪያ ላይ አዳዲስ የቁጥጥርና የገደብ ህጎችን ማዘጋጀቱ ያስቆጣቸው ሰዎች ብዙ አማራጮችን እየፈጠሩ ነው - ለምሳሌ፣ አንድ የዩኒቨርስቲ ተማሪ፣ የሽጉጥ ንድፍ ሰርቶ በኢንተርኔት አሰራጭቷል። ይሄኛው ሽጉጥ 400 ጥይቶችን በመተኮስ በተግባር የተሞከረ ሲሆን፣ ከ400 ሺ በላይ ሰዎች የሽጉጡን ንድፍ ከኢንተርኔት ወስደዋል። የአሜሪካ ነገር፣ አጃኢብ ነው።

አውሮፕላኖች በሚንደረደሩበት አውላላ ሜዳና ከፍተኛ ጥበቃ በሚደረግበት ኤርፖርት፣ የጥይት ድምፅ ሳይሰማ የተዘረፈው የ50 ሚሊዮን ዶላር አልማዝ፣ ከሶስት ወር የፖሊስ ክትትል በኋላ፣ ሰሞኑን ዱካው ተገኘ። ዝርፊያውን የፈፀሙ ስምንት ሰዎችን ከነተባባሪዎቻቸው ለመያዝና የተዘረፈውን አልማዝ ለማስመለስ በርካታ የአውሮፓ አገራትን ያዳረሰ ክትትል ሲያካሂዱ የከረሙ መርማሪዎች፣ በጣሊያን፣ በቤልጄምና በቱርክ ውጤት ቀንቷቸዋል። የካቲት 10 ቀን ከምሽቱ ሁለት ሰዓት ነው በቤልጄም ዋና ከተማ ከሚገኘው የብራስልስ ኤርፖርት አልማዙ የተዘረፈው። ከኤርፖርቱ አጠገብ፣ ጅምር የህንፃ ግንባታ ውስጥ ተደብቀው ያመሹት ስምንቱ ዘራፊዎች፤ የኤርፖርቱን አጥር ሲተረትሩ ማንም እንዳያያቸው ተጠንቅቀዋል። ወደ ውስጥ ከገቡ በኋላ ግን፣ በድብቅ ለመሽሎክሎክ አልሞከሩም። በተተረተረው አጥር ሁለት ጥቋቁር መኪኖችን እያሽከረከሩ ወደ አውሮፕላን መንደርደሪያው አመሩ።

ስምንቱ ዘራፊዎች እንደ ፖሊስ ለብሰው መሳሪያ ታጥቀዋል። በእርግጥ መሳሪያቸው የቤልጄም ፖሊሶች የሚጠቀሙበት አይነት ሳይሆን ክላሺንኮቭ ነው። ግን ከርቀት ይህንን ለይቶ የሚያስተውል አይኖርም። የፖሊስ ታርጋ የተለጠፈባቸው ሁለቱ ጥቋቁር መኪኖች፣ ኮፈናቸው ላይ ሰማያዊ የፖሊስ መብራቶች ተተልክሎላቸዋል። ማንም አላስቆማቸውም። በቀጥታ የአውሮፕላን መንደርደሪያዎችን እያቆራረጡ፣ ወደ ስዊዘርላንድ ለመብረር የተዘጋጀች መካከለኛ አውሮፕላን ጋ ደረሱ። ሌላ መኪና ለትንሽ ቀድሟቸዋል። ከእቅዳቸው ዝንፍ ያለ ነገር የለም። ከነሱ ቀድሞ የደረሰው መኪና፣ እንደ ካዝና በጠነከሩ ብረቶች የተሰራ የውድ እቃዎች ማመላለሻ ነው - ውድ የአልማዝ ጠጠሮችን ወደ አውሮፕላኑ የሚያደርስ። የመኪናው በር ተከፍቶ፣ እፍኝ እፍኝ የማይሞሉ 130 የአልማዝ ከረጢቶች ወደ አውሮፕላኑ ለማስገባት… ከዚያም አውሮፕላኑ ተነስቶ ለመብረር፣ ከ15 ደቂቃ በላይ መዘግየት እንደሌለበት ትዕዛዝ ተሰጥቷቸዋል። ዘራፊዎቹ ትክክለኛ መረጃ ባይኖራቸው ኖሮ፣ በትክክለኛው ሰዓት ባልደረሱ ነበር።

የአልማዝ ከረጢቶቹ ወደ አውሮፕላኑ ከገቡ በኋላ ለበረራ ሊነሳ ሲል ሁለት መኪኖች ከተፍ አሉ። የፖሊስ የደንብ ልብስ አድርገው፣ ፊታቸውን በጭንብል ሸፍነው፣ መሳሪያቸውን ወድረው ወደ አውሮፕላኑ የተንደረደሩት ዘራፊዎች፣ ፓይለቱንና የጥበቃ ሰራተኞችን በማስፈራራት የወርቅ ከረጢቶቹን ለመውሰድ ጊዜ አልፈጀባቸውም። በ20 ደቂቃ ውስጥ 50 ሚሊዮን ዶላር የሚያወጡ የአልማዝ እንቁዎችን ይዘው እንደአመጣጣቸው ተፈተለኩ - ግርግር ሳይፈጠር፣ የጥይት ድምፅ ብቻ ሳይሆን የሃይለ ቃል ድምፅ ሳይሰማ ዘረፋው ከመጠናቀቁ የተነሳ፤ ተሳፋሪዎቹ ምን እንደተፈጠረ አላወቁም። በረራው እንደተሰረዘና ዘረፋ እንደተፈፀመ ሲነገራቸው ማመን አልቻሉም ነበር። ስምንቱን ዘራፊዎች ከነተባባሪዎቻቸው ለመያዝ በበርካታ የአውሮፓ አገራት ለሶስት ወራት ሲካሄድ የቆየው የፖሊስ አደን፣ በዚህ ሳምንት በከፊል ውጤታማ ሆኗል።

ከዘራፊዎቹ መካከል አንዱ በጣሊያን ከ8 ተጠርጣሪ ተባባሪዎች ጋር የተያዘ ሲሆን፤ በስዊዘርላንድ ሌሎች ተባባሪዎች በቁጥጥር ስር ሲውሉ የተወሰነው ያህል አልማዝም ተገኝቷል። በቤልጄም ደግሞ ከሃያ በላይ ሰዎች ታስረዋል። በኤርፖርቱ የተፈፀመው ዝርፍያ፣ በታሪክ ከተመዘገቡ ትልልቅ የአልማዝ ዝርፊያዎች መካከል በሁለተኛ ደረጃነት የሚጠቀስ ቢሆንም፤ አልማዝን ማጓጓዝ ግን ለቤልጄም ኤርፖርቶች የእለት ተእለት ስራ ነው። በአለማችን ለገበያ ከሚቀርቡ የአልማዝ ጌጣጌጦች መካከል ግማሽ ያህሉ ቤልጄምን ሳይረግጥ አያልፍም - የአልማዝ ማዕድን ተሞርዶና ተጣርቶ አምሮበት የሚወጣው ቤልጄም ውስጥ በሚገኙ ኩባንያዎችና ባለሙያዎች ነው። በየእለቱ፣ ቤልጄም በአማካይ የ200 ሚሊዮን ዶላር አልማዝ ታስተናግዳለች።