Administrator

Administrator

    የአዘርባጃኑ ፕሬዚዳንት ኢሃም አሊየቭ የትዳር አጋራቸውን መህሪባንን ተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንት አድርገው መሾማቸውን ባለፈው ማክሰኞ በይፋ ማስታወቃቸውን አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
   ፕሬዚዳንቱ የ52 አመት ዕድሜ ያላቸውን ባለቤታቸውን በአገሪቱ የስልጣን እርከን ሁለተኛ ደረጃን በሚይዘውና ባለፈው መስከረም ወር ላይ በጸደቀው አዲሱ የተቀዳሚ ምክትል ፕሬዚዳንትነት ቦታ ላይ ማስቀመጣቸው ብዙዎችን እያነጋገረ እንደሚገን የገለጸው ዘገባው፣ ዘገባው ገልጧል፡፡ ባለፈው መስከረም ወር
ላይ በተከናወነው ህዝበ ውሳኔ በአገሪቱ የህገ መንግስት አንቀጾች ላይ ማሻሻያ መደረጉን ያስታወሰው ዘገባው፣
የፕሬዚዳንቱን የስልጣን ዘመን ከአመስት አመታት ወደ ሰባት አመታት ማሳደጉ፣ ከ14 አመታት በፊት የአባታቸውን ቦታ ተክተው አገሪቱን መምራት የጀመሩት ፕሬዚዳንት አሊየቭ ከስልጣን ላለመውረድ የያዙት አቋም መገለጫ ነው በሚል መተቸቱንም አክሎ ገልጧል፡፡
   በምክትል ፕሬዚዳንትነት የተሾሙት መህሪባን በህክምና ሙያ ከዩኒቨርሲቲ መመረቃቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ከዚህ ቀደም በህግ አውጭነት መስራታቸውንና የአንድ በጎ አድራጎት ድርጅት ሃላፊ ሆነው ማገልገላቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡
    ገና የ19 አመት ወጣት ሳሉ ከፕሬዚዳንት ኢሃም አሊየቭ ጋር ትዳር የመሰረቱት መህሪባን፣ በረጅም አመታት የትዳር ቆይታቸው ሁለት ሶቶች እና አንድ ወንድ ልጅ ማፍራታቸውን ዘገባው አክሎ ገለጧል፡፡

     ደቡብ ኮርያ በሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት ከአለማችን አገራት የመጀመሪያውን ደረጃ መያዟን ኦፕንሲግናል የተባለው የቴሌኮም መረጃ ተቋም ሰሞኑን ያወጣውን የጥናት ውጤት ጠቅሶ ሲቢሲ ኒውስ ዘግቧል። ተቋሙ በ87 የአለማችን የተለያዩ አገራት የ2016 የፈረንጆች አመት የሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት ዙሪያ ባደረገው ጥናት፣ ከአለም አንደኛ ደረጃን በያዘቺው ደቡብ ኮርያ የሞባይል ኢንተርኔት ፍጥነት በሰከንድ 37.54 ሜጋ ባይት እንደሚደርስ አስታውቋል፡፡
በሰከንድ 34.77 ሜጋ ባይት ፍጥነት ያለባት ኖርዌይ በሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት ሁለተኛ ደረጃን መያዟን የጠቆመው ዘገባው፣ ሃንጋሪ በ31.04 ሜጋ ባይት በሰከንድ ፍጥነት ሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጧን እንዲሁም ሲንጋፖር እና አውስትራሊያ በቅደም ተከተላቸው አራተኛና አምስተኛ ደረጃን መያዛቸውን ገልጧል፡፡
በጥናቱ ከተካተቱት የአፍሪካ አገራት በሞባይል ኢንተርኔት ፍጥነት አንደኛ ደረጃን የያዘቺው ደቡብ አፍሪካ ስትሆን፣ በሰከንድ 9.93 ሜጋ ባይት ፍጥነት ያላት አገሪቱ ከአለማችን አገራት ደግሞ የ48ኛ ደረጃን ይዛለች ተብሏል፡፡

     የናዚው መሪ አዶልፍ ሂትለር በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች እንዲገደሉ ትዕዛዝ አስተላልፈውበታል የተባለው ተንቀሳቃሽ ስልክ፣ በአሜሪካ ሜሪላንድ ውስጥ በተካሄደ ጨረታ 195 ሺህ ፓውንድ መሸጡ ተዘግቧል፡፡
የሂትለር የጥፋት ሞባይል ተብሎ የሚጠራውና ከ70 አመታት በላይ ዕድሜ እንዳለው የተነገረለት ይሄው ቀይ ቀለም ያለው ስልክ፣ በስተጀርባው የሂትለር ስም፣ የንስር ምስል እና የስዋስቲካ ምክልት እንዳለበት የዘገበው ቢቢሲ፣ ስሙ ያልተገለጸ ተጫራች በስልክ ባቀረበው የመወዳደሪያ ዋጋ አሸንፎ እንደገዛው ገልጧል፡፡
ብርጋዴር ጄኔራል ራልፍ ራይነር የተባሉ እንግሊዛዊ የጦር መሪ እ.ኤ.አ በ1945 በርሊን ውስጥ የሚገኘውን የሂትለር ምሽግ በጎበኙበት ወቅት፣ ይሄው ታሪካዊ ስልክ ከሩስያ የጦር መኮንኖች በስጦታ መልክ እንደተበረከተላቸውም ዘገባው አስታውሷል፡፡

በምርጫ ቢሸነፉም ስልጣኔን አልለቅም ብለው ለሳምንታት ካንገራገሩ በኋላ በተደረገባቸው ጫና አገራቸውን ጥለው የተሰደዱት የቀድሞው የጋምቢያ ፕሬዚዳንት ያያ ጃሜህ ከአገሪቱ ካዘና ያለአግባብ የዘረፉት ገንዘብ 1 ቢሊዮን ዶላር ያህል መድረሱን አዲሱ የአገሪቱ መንግስት አስታወቀ፡፡
አዲሱ የአዳማ ባሮው መንግስት ሚኒስትሮች ያወጡትም መረጃ ጠቅሶ ዘ ጋርዲያን እንደዘገበው፣ ተሰናባቹ ያያ ጃሜህ ከተለያዩ የአገሪቱ የመንግስት ተቋማት በየሰበብ አስባቡ ያለ አግባብ ለግል ጥቅማቸው ያዋሉት ገንዘብ በድምሩ 1 ቢሊዮን ዶላር ያህል መድረሱ በምርመራ ተረጋግጧል፡፡
ጃሜህ ከማህበራዊ ዋስትና፣ ከስፖርት እና ከቴሌኮም ድርጅቶች ብቻ 50 ሚሊዮን ዶላር ዘርፈዋል፤ ለግል አውሮፕላናቸው ግዢ ያለ አግባብ ከመንግስት ካዘና 4.5 ሚሊዮን ዶላር ወጪ ተደርጓል፣ እጅግ በርካታ ገንዘብም ያለ አግባብ ለግል ጥቅማቸው እንዲውል ተደርጓል ብሏል ዘገባው፡፡
ከአገሪቱ የማህበራዊ ዋስትና ካዘና ወጪ የተደረገ 40 ሚሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ የት እንደገባ አለመታወቁን የጠቆመው ዘገባው፣ ገንዘቡ በጃሜህ ኪስ ውስጥ ሳይገባ አይቀርም ተብሎ መጠርጠሩንና ቅንጦት ወዳጁ ጃሜህ በየሰበብ አስባቡ ደጋፊዎቻቸውን ለማስደሰት ባደረጓቸው የእራት ግብዣዎችና የቅንጦት ተግባራት 67 ሺህ ዶላር ያህል ወጪ መደረጉም ተነግሯል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን ተመድ ለተጠቀሱት አራት አገራት የሚያስፈልገውን 4.4 ቢሊዮን ዶላር ለማሰባሰብ ያደረገው ጥረት ይህ ነው የሚባል ውጤት አለማግኘቱንና እስካሁን ድረስ ማግኘት የቻለው 90 ሚሊዮን ዶላር ያህል ብቻ መሆኑን የጠቆሙት ዋና ጸሃፊው፣ አለማቀፉ ማህበረስብ በአፋጣኝ የድጋፍ እጁን እንዲዘረጋ ጠይቀዋል፡፡

   4.4 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል፣ የተገኘው 90 ሚሊዮን ዶላር ብቻ ነው

      አለማቀፉ ማህበረሰብ አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ርብርብ ካላደረገ በስተቀር፣ በተለያዩ አራት የአለማችን አገራት ውስጥ የሚገኙ 20 ሚሊዮን ያህል ሰዎች ለርሃብ አደጋ ሊጋለጡ ይችላሉ ሲል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባለፈው ረቡዕ አስጠንቅቋል፡፡
በደቡብ ሱዳን ሁለት ግዛቶች 100 ሺህ ሰዎች የርሃብ ተጠቂ መሆናቸውን ከቀናት በፊት በይፋ ያስታወቀው የተመድ ዋና ጸሃፊ አንቶኒዮ ጉቴሬስ፣ በሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች እንዲሁም በሶማሊያ፣ የመንና ናይጀሪያ በመጪዎቹ ስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ የከፋ ርሃብ ሊከሰት እንደሚችል አስጠንቅቀዋል፡፡ ከከፋ ድርቅና ከእርስ በእርስ ግጭቶች ጋር ተያይዞ በተጠቀሱት አገራት ይከሰታል ተብሎ የሚጠበቀውን የርሃብ አደጋ ለመከላከል አለማቀፉ ማህበረሰብ በመጪዎቹ ሶስት ሳምንታት ውስጥ ከፍተኛ ርብርብ በማደረግ 4.4 ቢሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ ማሰባሰብ እንዳለበትም ዋና ጸሃፊው ተናግረዋል፡፡
7.3 ሚሊዮን ያህል የመናውያን አስቸኳይ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል ያለው ተመድ፣ በደቡብ ሱዳን 5 ሚሊዮን ያህል ዜጎች የምግብ እርዳታ እንደሚፈልጉ፤ በሰሜን ምስራቃዊ ናይጀሪያ 5.1 ሚሊዮን ህዝብ የምግብ እጥረት ተጠቂ እንደሆነ፤ 2.9 ሚሊዮን ሶማሊያውያን አስቸኳይ የምግብ እና የሰብዓዊ እርዳታ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸውም ገልጧል፡፡
ይሄም ሆኖ ግን ተመድ ለተጠቀሱት አራት አገራት የሚያስፈልገውን 4.4 ቢሊዮን ዶላር ለማሰባሰብ ያደረገው ጥረት ይህ ነው የሚባል ውጤት አለማግኘቱንና እስካሁን ድረስ ማግኘት የቻለው 90 ሚሊዮን ዶላር ያህል ብቻ መሆኑን የጠቆሙት ዋና ጸሃፊው፣ አለማቀፉ ማህበረስብ በአፋጣኝ የድጋፍ እጁን እንዲዘረጋ ጠይቀዋል፡፡

 የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን በቀድሞ አትሌቶች በሚንቀሳቀስበት አዲስ ምዕራፍ ውስጥ ከገባ 6 ወራት ተቆጥረዋል፡፡ ፌደሬሽኑ በኢትዮጵያ ስፖርት  ከሚንቀሳቀሱ መሰል ተቋማት በተሟላ በጀትና የገቢ አስተማማኝነት  ተጠቃሽ ነው፡፡ በስፖርቱ ያለፉ የቀድሞ አትሌቶች ወደ  አመራር መምጣታቸው ወደ የላቀ ምዕራፍ እንደሚያሸጋግረው ታምኖበት ነው።  በአደረጃጀትና በአሠራር የሚነሱት ጉድለቶች መሻሻላቸውም ተጠብቋል፡፡ ቀደም ሲል በአትሌቲክስ መሰረተልማቶች፤ በውድድሮች፤ በሆቴል፤ በሪል ስቴት እና ሌሎች የኢንቨስትመንት መስኮች የሚንቀሳቀሱ  አትሌቶች  በስፖርቱ አስተዳደር ለውጥ ለመፍጠር እና ለማገልገል አቋም ይዘው መነሳታቸው ብዙ ተስፋዎችን ፈጥሯል።  ይህ የስፖርት አድማስ ሀተታ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኑ ባለፉት 6 ወራት ያከናወናቸውን አበይት ተግባራት ይዳስሳል፡፡ ፌዴሬሽኑ የከፈታቸው አዳዲስ ምእራፎች፤ የብሄራዊ ቡድን ምርጫዎች፤ በተለያዩ ጊዜያት ከብሄራዊ ቡድን አትሌቶች እና አሰልጣኞች፤ ከሌሎች አትሌት ማናጀሮች፣ አሰልጣኞች፤ ክለቦች ተወካዮችና አትሌቶች ጋር ያካሄዳቸው የምክክር መድረኮች፤ የውይይት አጀንዳዎች ላይ ያተኩራል፡፡
የፌደሬሽኑ ታሪክና ያለበት ደረጃ
በኢትዮጵያ የአትሌቲክስ ስፖርት ከ137 ዓመታት በፊት በትምህርት ቤቶችና በወታደራዊ ካምፖች በመዘውተር  እንደተጀመረ ይነገራል፡፡ ስፖርቱን በበላይነት የሚመራው ተቋም ‹‹ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን›› በሚል መጠሪያ የተመሰረተው ከ68 ዓመታት በፊት ነው። በዓለም አቀፉ የስፖርት ህግ መሠረት በአንድ ሀገር በአንድ የስፖርት ዓይነት ሊኖር የሚችለው አንድ ሀገር አቀፍ ፌዴሬሽን ብቻ ነው፡፡ በፌደሬሽኑ ድረገፅ የተቀመጠው ታሪካዊ ዳራ እንደሚያወሳው ፌዴሬሽኑ የሀገሪቱን ሕግና ደንብ ጠብቆ በሕዝብ፣ በመንግስትና በድርጅቶች ድጋፍ የሚንቀሳቀስ ሀገር አቀፍ፣ አህጉር አቀፍና ዓለም አቀፍ የአትሌቲክስ ተግባራትን የሚያከናውንና ከአጠቃላይ የህብረተሰቡ አትሌቲክስ ስፖርት እንቅስቃሴ በመነሳት በተለይ የወጣቱን ትውልድ ግንዛቤና ተሳትፎ በማጠናከር የላቀ ችሎታ ያላቸው ምርጥ ስፖርተኞች እንዲፈሩ በማድረግ በአለም አቀፍ ደረጃ የአገራችንን ተወዳዳሪነትና ተጠቃሚነት ማስፋት በሚል አጠቃላይ ዓላማ የተቋቋመ ማህበር ነው፡፡
እንደፌደሬሽኑ ድረገፅ ሃተታ ከአህጉርና ዓለም አቀፍ ግንኙነት አኳያም  ፌዴሬሽኑ ከዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር፣ ከአዲዳስ ኩባንያ፣ ከአፍሪካ አትሌቲክስ ኮንፌዴሬሽን፣ ከምስራቅ አፍሪካ አትሌቲክስ ሪጅንና ከአቻ ዓለም አቀፍና አህጉር አቀፍ ተቋማት ጋር መልካም የሚባልና በአርዓያነት ሊጠቀስ የሚችል ግንኙነት ያደርጋል፡፡ የዓለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር (IAAF) ፤በአፍሪካ አትሌቲክስ ኮንፌዴሬሽን (CAA) እና በምሥራቅ አፍሪካ አትሌቲክስ ሪጅን (EAAR) አባልነቱ የሚንቀሳቀስም ነው፡፡
ፌዴሬሽኑ በየዓመቱ በሚያካሂዳቸው ከ10 በላይ የሃገር ውስጥ ውድድሮች ላይ የመላ ሃገሪቱ ክልሎች፣ ከተማ አስተዳደሮችና ክለቦች እንዲሳተፉ ያደርጋል። አትሌቶች ከሚያገኙት የቡድን ሽልማት፣ ከአትሌት ማናጀሮች ዓመታዊ ክፍያ፣ ከዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማሕበር፣ ከሕንፃ ኪራይ እና ከአዲዳስ ኩባንያ በድምሩ በየዓመቱ ከ40 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ሲኖረው፤ ከፌደሬሽኑ ገቢዎች ትልቁ ከአዲዳስ ኩባንያ ጋር ያለው የስፖንሰርሽፕ ስምምነት ሲሆን ለስምንት ዓመት በሚቆየው ውል፤ ለአንድ ዓመት 1.5 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያገኝ፤ ቦነሶችን ጨምሮ በአጠቃላይ ከ30 ሚሊዮን ብር በላይ ነው፡፡ በሌላ በኩል በየውድድር ዘመኑ ውስጥ በፌደሬሽኑ ስር ለተካሄዱት ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ውድድሮች፣ በተለያዩ የመሰረተልማት ስራዎች፤ ለፌዴሬሽኑ ሰራተኞችና አሰልጣኞች ደመወዝና ስራ ማስኬጃ፣ ለትምህርትና ስልጠና፣ ለብሔራዊ ቡድን አትሌቶች ድጎማ፣ ለማርኬቲንግና ኮሚዩኒኬሽን፣ ለስፖርት ዕቃዎች ግዢ፣ ለሜዳና ለሕንፃ ጥገና፣ ለድጋፍ ለማበረታቻ እና ሽልማት እንዲሁም ሌሎች ለታቀዱ ስራዎች ማስፈፀሚያ እስከ 43 ሚሊዮን ብር ወጭ አለበት፡፡
የአዲሱ አመራር ልዩ አቅጣጫዎች
በሻለቃ ኃይሌ ገብረስላሴ ፕሬዝዳንትነት የሚመራው አዲሱ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ከፌዴሬሽኑ ጽ/ቤት ሰራተኞች፣ ከአትሌት ተወካዮችና ከአትሌቲክስ አሰልጣኞች ጋር የትውውቅ መድረክ በማመቻቸት ስራውን ጀምሯል፡፡   በአትሌቲክሱ አጠቃላይ ጉዳዮች ዙሪያ ከአትሌት ተወካዮችና ከአሰልጣኞች ጋር ጥልቅና ጠቃሚ ውይይቶች በማድረግ ካለፉት አስተዳደሮች የተለየ ሆኗል፡፡ በቀጣይ 3 እና 4 አመታት በአትሌቲክሱ ኢትዮጵያን በተሻለ ውጤታማ ለማድረግ ያተኩሯል፡፡ ህፃናትን፣ ታዳጊዎችን፣ ወጣቶችንና አዋቂዎችን ከት/ቤቶች፣ ከፕሮጀክቶች፣ ከክለቦች፣ ከክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ጋር  ለማስተሳሰር የሚጥር ነው፡፡ በኢትየጵያ አትሌቲክስ የተዘበራረቀውን የስልጠና  የውድድር ሂደቶች ወጥ ማድረግ ይፈልጋል።  የአትሌቶችና የአሰልጣኞች - የአትሌቶችና የአትሌቶች - የአሰልጣኞችና የአሰልጣኞች የእርስ በርስ ግንኙነቶች በተሻለ ደረጃ ማስተካከል ይፈልጋል።  የእድሜ ማጭበርበር ለማስቀረትና በአትሌቲክስ ስፖርቶች ያለውን የተሳትፎ ውስንነት ለመለወጥም ተነስቷል። በአዲስ አበባ ላይ የሚታየውን የአትሌቶች ክምችትና ስልጠና ወደ ክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች እንዲቀየር  ለአሰልጣኞች፣ ለክለቦች፣ ለክልሎችና ከተማ አስተዳደሮች ግንዛቤ በመፍጠር ተንቀሳቅሷል።  የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት ሻለቃ ኃይሌ ገብረሥላሴ  ባንድ ወቅት እንደተናገረው ደግሞ … ሙያተኞች በየክልሎች ተዘዋውረው  ጥናቶችን የሰሩ ሲሆን፤ ከሩጫ ባሻገር ባሉ የአትሌቲክስ ስፖርቶች ከፍተኛ አቅም ያላቸው አካባቢዎች ተለይተው በመታወቃቸው፤ የመፍትሔ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ ሊሰራበት ነው። የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት እና ሌሎች የስራ አስፈፃሚ አባላት በየጊዜው የምክክር መድረኮችን በማዘጋጀት እየተንቀሳቀሱም ናቸው። በእነዚህ መድረኮች የብሔራዊ ቡድን አሰልጣኞችና አትሌቶች፣ የክለብ አትሌቶችና አሰልጣኞች፣ የአትሌቶች ማናጀሮችና ተወካዮች እንዲሁም የሚዲያ ባለሙያዎች እየተሳተፉ ናቸው፡፡  ፌዴሬሽኑ በየምክክር መድረኮች በተለያዩ የስፓርት አጀንዳዎች ዙርያ ግልፅ ውይይት በማድረግ ለማስተማር፣ ለማሳወቅ የሚሰራበት ሁኔታ ለስፖርቱ እድገትና ለውጥ ቅድሚያ ትኩረት መስጠቱን ያመለክታል፡፡ በየመድረኩ የአትሌቲክሱን ባለድርሻ አካላት የሚመራባቸውን አዳዲስ አሰራሮችና መመርያዎች በማስተዋወቅ እና በውይይት በማዳበር እየሰራ አዳዲስና ልዩ አቅጣጫዎችን ይዟል፡፡
የብሄራዊ ቡድኖች ምርጫና ከአዲስ አበባ ውጭ ዝግጅት
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የ2009 ዓ.ም የብሄራዊ ቡድን አትሌቶችና አሰልጣኞች ምርጫ በማካሄድ በአፍሪካ እና በዓለም አቀፍ ውድድሮች ኢትዮጵያ ለሚኖራት ተሳትፎ የሚደረጉ ዝግጅቶችን አጠናክሯል፡፡ ብሄራዊ ቡድኖች ዝግጅቶቻቸውን ከአዲስ አበባ ውጭ እንዲደርጉ መወሰኑ ሌላው አዲስ አቅጣጫ ሲሆን፤ በዋናነትም አሰላ የሚገኘው የጥሩነሽ ዲባባ ማሠልጠኛ ማዕከል የመጀመርያው ተመራጭ ሆኖበታል፡፡ ፌደሬሽኑ  በስልጠና ፤ በዉድድር እና በእድገት ላይ በማተኮሩም ከ50 የማያንሱ የብሔራዊ ቡድን አሠልጣኞችና ተያያዥነት ያላቸው ሙያተኞች በመፈፀም ወደ ስራ ገብቷል፡፡ ከከፍተኛ የአሰልጣኝነት ሹመቶቹም መካከከል ዶ/ር ይልማ በርታ የፕሮጄክቶች፣የማዕከላት፣የአካዳሚ፣ የክለቦች እንዲሁም የብሔራዊ ቡድን እና የማናጀሮች ስልጠና ዋና አስተባባሪ፤ መላኩ ደረሰ፤ የማዕከላት፣ የፕሮጄክቶች እና የአካዳሚ ስልጠና ክትትል፤ ትዕዛዙ ዉብሸት፤ የክለቦች ስልጠና ክትትል እንዲሁም መሰረት መንግስቱ፤ የማኑዋል ዝግጅት አስተባባሪ መሆናቸውን መጥቀስ ይቻላል፡፡
የብሄራዊ ቡድን  አትሌቶችን በተለያዩ የውድድር መደቦች የመረጠው ደግሞ መስፈርቶቹን በግልፅ በማሳወቅ ነበር፡፡ በ2009 ዓ.ም የብሔራዊ ቡድን አትሌቶች የመምረጫ መስፈርት
በ2008 ዓ.ም በአህጉርና በዓለም ዓቀፍ ዉድድሮች የተሻለ ዉጤት ያስመዘገቡ፤ በ2008 ዓ.ም በአጭር ርቀት እና የሜዳ ተግባራት ከ1ኛ-2ኛ የወጡ፤ በ2008 ዓ.ም በመካከለኛ እና በረጅም ርቀት ስልጠና ምድቦች ከ1ኛ-3ኛ የወጡ፤ በአሰልጣኝ እይታ፤ ብቁ የሆኑት ተመልምለዋል፡፡
አክሳሪው የዶፒንግ ቀውስ
የዓለም አቀፍ የፀረ አበረታች ንጥረ ነገሮች ኤጀንሲ (ዋዳ) ኢትዮጵያን በዶፒንግ ቀውስ  ከሚገኙ አምስት አገራት ተርታ እንደፈረጃት ይታወቃል፡፡ አዲሱን ፌደሬሽን እየተፈታተኑ ከሚገኙ አሳሳቢ ሁኔታዎች ዋንኛው ነው፡፡ በአገር ደረጃ በተቋቋመው ብሔራዊ የፀረ አበረታች ንጥረ ነገሮች ኤጀንሲ (ናዶ) አማካኝነት የመጀመርያው ግዙፍ ምርመራ የተካሄደው በቅርቡ ነው፡፡ ከአንድ መቶ በላይ አትሌቶች የደምና የሽንት ናሙና ሰጥተዋል፡፡ ናሙናዎቹ ወደ እውቅና ወደተሰጠው የኳታር  የምርመራ ማዕከል ቢላክም ተቋሙ ከጥራት ጋር በተያያዘ  በመታገዱ በፈረንሣይ የሚገኘው የምርመራ ማዕከል በምትኩ ተመርጦ ናሙናዎችን ተረክቦ እየመረመራቸው ነው፡፡ በዓለም አቀፉ ተቋም ዋዳ  በተሰጠው መመርያ  እስከ 200 ለሚደርሱ የኢትዮጵያ አትሌቶች ምርመራው በተያዘው የውድድር ዘመን ይቀጥላል፡፡ የዶፒንግ ምርመራዎቹ ሙሉ ወጪ የሚሸፈነው በኢትዮጵያ መሆኑ ቀውሱ ኪሳራ ሊያከትል እንደሚችል ያመለከተ ሲሆን፤  ለአንድ አትሌት የዶፒንግ ምርመራ እስከ 500 ዶላር እየተከፈለ ይገኛል፡፡ በፀረ - ዶፒንግ እንቅስቃሴ ዙሪያ የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን ለውጭ ሃገርና ለሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን አካላት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ፕሬዝዳንቱ ሻለቃ አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ በአጠቃላይ እንዳመለከተው፤ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ አትሌት ከአበረታች መድሃኒቶችና ቅመሞች አጠቃቀም እና ድርጊቶች ጋር ተያይዞ በIAAF 4 አመት እገዳ ከተጣለበትና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አባል ከሆነ ከአባልነት እስከ መጨረሻ ይታገዳል፡፡ አባል ካልሆነ ደግሞ እስከ መጨረሻ የብሔራዊ ቡድኑን አይቀላቀልም። በተጨማሪም ኢትዮጵያን ወክሎ በማንኛውም አይነት ሃገር አቀፍ፣ አህጉር፣ ዓለም አቀፍ እንዲሁም ማንኛውም ኢንተርናሽናል ውድድር መሳተፍ አይችልም፡፡ ዶፒንግን በተመለከተ ፌዴሬሽኑ ምንም አይነት ድርድር (ይቅርታ) ባይኖረውም፤ ለእውነተኛ እና ንፁህ አትሌቶቻችን መብት  በማንኛውም ሁኔታ እስከ መጨረሻ ድረስ ይሟገታልም ተብሏል፡፡
በዜግነት ቅየራ ላይ…
የዓለም አቀፍ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማኅበር የሆነው አይ.ኤ.ኤ.ኤፍ ከሁለት ሳምንት በፊት ባወጣው መግለጫ የኢትዮጵያና የኬንያ አትሌቶች ዜግነት ቀይረው ለማንኛውም አገር  እንዳይሮጡ ማገዱን አስታውቆ ነበር። ውሳኔው ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በከፍተኛ ሁኔታ የጨመረውን የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች ስደት እና ዜግነት ቅየራ የሚከላከል መሆኑ ተገልጿል። የዜግነት ቅየራው የምስራቅ አፍሪካ አትሌቶች በአገር አቋራጭ፤ በመካከለኛና በረጅም ርቀት የትራክ ውድድሮች እና በጎዳና ላይ ሩጫዎች የኢትዮጵያና የኬንያ አትሌቶች የበላይነት በማብዛት በውድድሮቹ ህልውና ላይ ተፅእኖዎች እየፈጠረ ቆይቷል፡፡
የማናጀሮች እና የአትሌቶች የስነምግባር ጉድለት፤ የስራ ውል
በተለያዩ ደረጃዎች በኢትዮጵያ አትሌቲክስ በአትሌት ማናጀርነትና ተወካይነት በመንቀሳቀስ ላይ በሚገኙት የስፖርቱ ባለድርሻ አካላት ፌደሬሽኑ ብዙ ችግሮች እየተፈጠሩበት ይገኛል፡፡ በርካታ ማናጀሮች በፌዴሬሽኑ በኩል የሚሰጣቸውን መመርያዎች ለማክበር እየተሳናቸው መቀጠሉ ፌደሬሽኑን አሳስቦታል።  ከሳምንት በፊት በተካሄደው 34ኛው የጃን ሜዳ ኢንተርናሽናል አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ የተከሰቱ ሁኔታዎች በናሙናት መጥቀስ ይቻላል፡፡ ፌዴሬሽኑ በዚሁ አገር አቋራጭ ሻምፒዮና ላይ ክለቦችና ማናጀሮች አትሌቶቻቸውን በንቃት እንዲያሳትፉ ቢያሳስብም አትሌቶቻቸውን ወደተለያዩ የውጭ አገር ውድድሮች በመላክ ማሳሰቢያውን ያላከበሩት ጥቂት ማናጀሮች አይደሉም፡፡  ‹‹በፌዴሬሽኑ በኩል የቅጣት ርምጃዎችን መውሰድ ቀላል ነገር ነው፡፡››…የሚለው ሻለቃ ኃይሌ ገ/ስላሴ፤ ‹‹ማናጀሮች የምናወጣቸውን መመርያዎች እና ደንቦች በተደጋጋሚ እየጣሱ በመሆናቸው ወደ ቅጣት ውሳኔዎች ለመግባት እያስገደደን ነው›› ብሏል። በአህጉራዊ ዓለም አቀፋዊ ውድድሮች ላይ አገርን  ወክለው የሚሳተፉ የብሄራዊ ቡድን አባላት ሙያዊ ስነምግባሮችን ማክበር እንዳለባቸው፤ የተለያዩ የፌደሬሽኑ  መመርያዎችን የማያከብሩ አትሌቶች፣ አሰልጣኞችና ማናጀሮች በብሔራዊ ቡድን  ውስጥ ይዞ መቀጠል እንደማቻ እና በአትሌቲክሱ እንቅስቃሴ ህጋዊ እውቅና እንደማኖራቸው ስራ አስፈፃሚዎቹ በየመድረኮቹ እያሳሰቡ ናቸው፡፡
በአትሌቶችና በማናጀሮቻቸው መካከል በሚፈፀሙ የስራ ውሎች ላይም ችግሮች እየተፈጠሩ ናቸው፡፡ በሁሉም የአትሌቲክስ ባለድርሻ አካላት የሚፈፀሙ ውሎች ባለመኖራቸው ንትርኮች በዝተዋል፡፡ በአትሌቶችና በማናጀሮቻቸው መካከል በሚፈፀሙ የስራ ውሎች በአግባቡ እንደ ሰነድ ተዘጋጅተው፤ በሚመለከታቸው አካላት  የፀደቁ መሆን ነበረባቸው፡፡ ይሁንና ይህን ሂደት ባልተከተሉ ውሎች ለፌዴሬሽኑ የሚቀርቡ አቤቱታዎች እና ክሶች እየበዙ መጥተዋል፡፡ በአይ.ኤ.ኤ.ኤፍ የተመዘገቡ የአትሌቶች ማናጀሮች ብቻ ከአትሌቶች ጋር ለመስራት እና ውል ለመፈፀም የሚችሉበት እውቅና እንደሚያገኙ የሚገልፁት የፌዴሬሽኑ ስራ አስፈፃሚዎች፤ ማናጀሮችና አትሌቶች ግልፅ የስራ ውል ፈርመው በማዘጋጀት ለፌደሬሽኑ ገቢ ማድረጋቸው በህጋዊነት ለመስራት ያስችላቸዋል ብለዋል፡፡
የዶፒንግ ምርመራ መርሃ ግብሮች አለመከበር
በየዓመቱ የሚመረጡት የብሔራዊ ቡድን አትሌቶች በአይ.ኤ.ኤ.ኤፍ እና በዋዳ ክትትል እየተደረገባቸው በየጊዜው የዶፒንግ ምርመራ ውስጥ ይገባሉ። ስለሆነም በተለያዩ የውድድር መደቦች ለብሄራዊ ቡድን የተመረጡ አትሌቶች ይህን ወሳኝ መርሀ ግብር ማክበር ይጠበቅባቸዋል፡፡ የአትሌቲክስ ፌዴሬሽን የስራ ኃላፊዎች እንደሚገልፁት ግን ብዙዎቹ አትሌቶች፤ አሰልጣኞች እና ማናጀሮቻቸው ይህን ሁኔታ በቂ ትኩረት ባለመስጠታቸው አላስፈላጊ ጥፋቶች እየፈጠሩ መሆኑ አሳስቧቸዋል፡፡ በዶፒንግ ምርመራውና የክትትል መመርያ መሰረት ለብሔራዊ ቡድን የተመረጡት አትሌቶች የ3 ወር መርኃ ግብራቸውን በዝርዝር በሚመዘግቡት ፎርም ያስታውቃሉ፡፡ ብዙ የኢትዮጵያ  አትሌቶች የመመዝገብ ችግር ባይኖርባቸውም በፎርም ላይ የመዘገቡትን መርሐ ግብር የማያከብሩ ሆነው ፌዴረሽኑን ለማያስፈልግ ትችት እያጋለጡት ናቸው፡፡  በቅርብ ጊዜ ከዚሁ ጋር ተያይዞ ያጋጠመውን ሁኔታ በምሳሌነት ማንሣት ይቻላል፡፡  22 የብሔር ቡድን አትሌቶች ስለእለት መርሃ ግብራቸው በመዘገቡት መረጃ መሰረት የአይ.ኤ.ኤ.ኤፍ እና የዋዳ ተወካዮች ድንገተኛ ምርመራ ሊያካሄዱ ወስነው የገጠማቸው ነው፡፡ 22ቱ አትሌቶች በስታድዬም እንገኛለን ብለው ፎርም የሞሉ ቢሆንም በቦታው የተገኘው አንድ አትሌት ብቻ ነበር፡፡ በአይ.ኤ.ኤ.ኤፍና ዋዳ የዶፒንግ ምርመራ እና ክትትል መመርያ ማንኛም አትሌት የ3 ወር መርሃግብሩን አለማክበሩ የሚያስቀጣው መሆኑን የሚያሳስበው ፌደሬሽኑ፤ ይህን ደንብ በተደጋጋሚ የሚተላለፉ አትሌቶች ቅጣት ሲወሰንባቸው ተዓማኒነት እያጎደለ የሚሄድ መሆኑ ያሳስበዋል፡፡
አሳሳቢዎች ውድድሮች በቻይና ምድር
የኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን እጅግ ካሳሰቡት ሁኔታዎች ሌላኛው በቻይና በሚዘጋጁ ውድድሮች ላይ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በህገወጥ ዝውውር እና ግንኙነቶች የጉልበት እና የመብት ብዝበዛ ውስጥ መግባታቸው ነው፡፡ በቻይና በሚዘጋጁ ውድድሮች ላይ አትሌቶች በብዛት እየተሳተፉ መሆናቸው ለስፖርቱ እድገት ሳይሆን ውድቀት በር እየከፈተ ነው በማለት የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚዎች ይናገራሉ፡፡ አትሌቶች ከፌደሬሽኑ እውቅና ውጭ ቻይና ውስጥ በሚዘጋጁ ውድድሮች መሮጥ ማብዛታቸው ብቻ አይደለም። በህገወጥ ደላሎችና እውቅና በሌላቸው ማናጀሮች የጉልበት ብዝበዛ እየተደረገባቸው፤ ገንዘባቸው እየተመዘበረ እና ለዶፒንግ እግሮች እያጋለጣቸው መሆኑ በፌደሬሽኑ በኩል ተረጋግጧል፡፡
በቻይና የሚዘጋጁ ውድድሮች ላይ  ለመሳተፍ የሚቻለው በፌደሬሽኑ ተመዝግቦ እውቅና ባገኘ ማናጀር ብቻ ነው፡፡ በህገወጥ ደላሎች እና የአትሌት ተወካዮች ነን በሚሉ ግለሰቦች ፌደሬሽኑ ሳያውቀው የሚደረጉ የውድድር ተሳትፎዎች ህገወጥ መሆናቸውን ፌደሬሽኑ አስገንዝቧል፡፡ ብዙሃነ እየተፈፀመ ነው ተብሏል፡፡ አትሌቶችን ለክፉ አደጋዎች ከሚያጋልጡ ሁኔታዎች የመጀመርያው በቻይና በሚደረጉ ውድድሮች የሚቀርቡት የ40ሺ እና የ60ሺ ዶላር የገንዘብ ሽልማቶች ሲሆኑ አትሌቶች  ስፖርቱ በማይፈቅደው መንገድ በ1 ወር ውስጥ ሁለት  ማራቶኖች ለመሮጥ፤ በ18 አመታቸው ውድድር ለማድረግና በዶፒንግ ቀውስ ውስጥ ለመግባት የሚዳርጋቸው ሆኗል፡፡ ፌዴሬሽን እንደሚያሳስበው ወደ ቻይና አትሌቶችን የሚልኩ ማናጀሮች የተመዘገቡና ህጋዊ እውቀና ያገኙ መሆን አለባቸው፡፡ ይህን ያልተገበረ ማንኛውም አትሌት ሆነ ማናጀር ኢትዮጵያ መወከል አይችልም፡፡ከወከለም የቅጣት እርምጃ ይጠብቀዋል፡፡

 የገጣሚ ዮና ውብሸት ግጥሞች የተካተቱበት ‹‹ጭጋግ ዘመኖች›› የግጥም መድበል ዛሬ ከቀኑ 8፡30 አምስት ኪሎ በሚገኘው የኢትዮጵያ ቅርስና ጥበቃ ባለስልጣን አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በምርቃት ስነ-ስርዓቱ ላይ እውቅ ገጣሚያንና ደራሲያን ስራዎቻቸውን እንደሚያቀርቡም ተገልጿል፡፡ ‹‹ጭጋግ ዘመኖች›› የፖለቲካ፣ ማህበራዊና ፍልስፍናዊ ጭብጦችን የሚዳስሱ ከ60 በላይ ግጥሞችን የያዘ ሲሆን በ90 ገፆች ተቀንብቦ፣ በ45 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

   በደራሲ አበቡ በሪሁን የተፃፈውና በማህበራዊ አኗኗር፣ የትዳርን በጎና እኩይ ገፅታዎች ዙሪያ የሚያሳየው ‹‹ያልነጠፈ ተስፋ›› ወጥ ልቦለድ መፅሀፍ ለንባብ በቃ፡፡ ሰዎች ከላይ ጥሩ መስለው ውስጣቸው እንዴት በተቃራኒው መጥፎ እንደሚሆን በዋና ገፀ ባህሪው ለማሳየት መጣሯ በመግቢያው ተገልጿል፡፡ ይህ መፅሀፍ በ263 ተቀንብቦ በመቶ ብርና በ50 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡

ላለፉት 50 ዓመታት በፎቶግራፍ ባለሙያነት የሰሩትና ባለፈው መስከረም 6 ቀን 2009 ዓ.ም በድንገተኛ ህመም ሀይወታቸው ያለፈው አቶ ተሾመ ንጉሴ ነገ ከቀኑ 10፡00 ጀምሮ በአዳማ ኩሪፍቱ ሪዞርት በተለያዩ ዝግጅቶች እንደሚዘከሩ የፕሮግራሙ አስተባባሪዎች ለአዲስ አድማስ ገለፁ፡፡ በዕለቱ የህይወት ታሪካቸውን የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልም ግጥምና የህይወት ታሪካቸው የሚቀርብ ሲሆን የፎቶግራፍ ስራዎቻቸውን ለእይታ በማቅረብም እንደሚዘከሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Sunday, 26 February 2017 00:00

ገቢና ወጪ - (ወግ)

  “መቼም ያለ ፈጣሪ መኖር የማይሆንልን ከሆነ … መቼስ ምን ማድረግ ይቻላል?” ብሎ ዝም አለ፤ የክሪስቶፈር ሂችንስን መፅሐፍ ከአዛውንቱ ተውሶ ሲያነብ የቆየው ወጣት፡፡ መፅሐፉን በእጁ ላይ ይዞ እየደባበሰው ነው፡፡
አዛውንቱ ወፍራሙን ጋቢያቸውን ለብሰው፣ በቀዝቃዛው የክረምት ጭጋግ ውስጥ ቆመዋል፡፡ ወጣቱ በአዛውንቱ ግቢ ውስጥ ከጎናቸው ቆሟል። እጁን በአክብሮት ከጀርባው አጣምሮታል፡፡ በእጁ ላይ መፅሐፉን ይዞ ይደባብሰዋል፡፡ አዛውንቱ ነባር ሳይንቲስትና ኢ-አማኒ ናቸው፡፡ ኢ -አማኒ ናቸው ይባልላቸዋል እንጂ የሚያምኑት የሌላቸው አይደሉም፡፡ ለምሳሌ በህይወት ያምናሉ፡፡ ባያምኑ እስከዚህ እድሜ ድረስ መኖር አይችሉም ነበር … ብሎ አሰበ ወጣቱ፤መፅሐፉን እየደባበሰ፡፡
“ያለ ፈጣሪ መኖር የማይሆንልን ከሆነ፣ የሚመጥነንን ፈጣሪ መፍጠር ነዋ!” አሉ አዛውንቱ። አፍንጫቸውን የማሸት ባህርይ አላቸው፡፡ በመደባበስ ብዛት መፅሐፉ በወጣቱ እጅ ላይ እንዳረጀው .. የአዛውንቱ አፍንጫ ደግሞ ከሌላው የፊታቸው ቅላት ተለይቶ ጠቁሯል፡፡
“ፈጣሪ ባይኖር ኖሮ ልንፈጥረው እንገደድ ነበር ---- እንዳለው ማለትዎ ነው?” አለ ወጣቱ፤ ከእርስዎ ባላውቅም በሚል ትህትና፡፡
“አዎ በትክክል … ግን ቮልቴር መፍጠር ያለብን ምን አይነቱን ፈጣሪ ነው ብትለው መልስ የለውም … እኔ ደግሞ የምለው መፍጠር የማትችለውን ፈጣሪ ለምን ወደዛ አትተወውም … ከአቅምህ በላይ ከሆነ … መተው አይሻልም?!” ብለው አፍንጫቸውን መፈተግ ቀጠሉ፡፡ ጣታቸው በአፍንጫቸው ቀዳዳ ገብቶም እንደማፅዳት ይልና፣ ከዛ ደግሞ ወደ ላይና ወደ ታች እየተመላለሰ መፈተጉን ይቀጥላል። የማሰላሰያ ጊዜ ለመግዛት የሚያደርጉት ሙከራ ሳይሆን አይቀርም ብሎ ወጣቱ ጠረጠረ፡፡ እሱም የራሱ የማሰላሰያ ቴክኒክ አለው፡፡ በልማድ ሁለት እጆቹን እያጨባበጠ መፈተግ ይቀናዋል፡፡ አሁን በእጆቹ መሀል ያለው መፅሐፍ ስለሆነ፣ የመፅሐፉ ገፆች ወደ መላላጥ ቀርበዋል፡፡
ወሬውን ወደ ሌላ አቅጣጫ ለመቀየር “ዛሬ ልደቴ ስለሆነ አንዳች ነገር ማድረግ አሰኝቶኛል” አለ ወጣቱ፤ መፅሐፉን ለአዛውንቱ እያቀበላቸው። ለመቀበል ፍላጎት ያላቸው አልመሰሉም፡፡ የተዘረጋው እጁ ተንከርፍፎ በአየር ላይ ቀረ፡፡
“ስንተኛ ዓመት ልደትህ ነው? … የሚገርም ነው፤ እኔ በአንተ እድሜ ሳለሁ ስለልደቴ ምንም አላውቅም ነበር፡፡ ለመወለድና ለልደት ቀን ከፍ ያለ ግምት እንዲኖር፣ የኑሮ ደረጃም ከፍ ማለት አለበት። … እኔ ወጣት ሳለሁ ዋነኛው ነገር ሚስት አግብቼ፣ ልጆች ወልዶ ማስተማር ነበር ቁም ነገሩ” ብለው ድንገት ዝም አሉ፡፡ ወደ ትዝታ፣ ወደ ኋላ ዘመን ሲሸመጥጡ … አፍንጫቸውን ተወት አደረጉት፡፡ ሀሳብ ከአፍንጫ ጋር ያለው ትስስር ጠንካራ መሆኑ ወጣቱን በድጋሚ ተሰማው፡፡
“አሁን አንተ የምታነበውን አይነት መፅሐፍ፣ እኔ ወጣት በነበርኩበት ጊዜ የማንበብ ፍላጎት አልነበረኝም፡፡ በዛ ዘመን የማምንበት ፈጣሪ መጠኔ ስለመሆኑ እርግጠኛ ነበርኩኝ፡፡ ፈጣሪና እኔ ተስማምተን ነበር የምንኖረው፡፡ ከመስማማታችንም በላይ በጥልቅ የምንነጋገር፣ የምንቀራረብ ይመስለኝ ነበር፡፡ ታውቃለህ አይደል፤ መስማማት ማለት ባለህበት መርገጥ ማለት ነው፡፡ … እኔና ፈጣሪዬ ባለንበት ብንረግጥም … ተፈጥሮና የህይወት ሂደት ግን ይለወጣል፡፡ … ለውጥ መጣ፡፡ የተማሪዎች እንቅስቃሴ ይዞ የመጣው ሀሊዮ፣ በእኔና በፈጣሪ መሀል አለመግባባትን ፈጠረ፡፡ የፈጣሪ ንግግር ለሚያድገው አእምሮዬ ጠበበኝ፡፡ ልክ የልጅነቴን ልብስ በሚያድገው አካላቴ ላይ አምጥተው እንዳጠቀለቁልኝ ጠበበኝ፤ … ጥበቱን ለማስፋት አንድም የበለጠ ሀይማኖተኛ መሆን አልያም … የጭንቅላቴን መጠን አስፍቼ የበለጠ ማሰብና ማወቅ ነበር ያለኝ አማራጭ፡፡ ከዚህ በላይ አማራጭ መኖሩን ለማወቅ ራሱ ማወቅና የአስተሳሰብን አድማስ ማስፋት … ቀዳሚ ግዴታዬ ነበር ..” … ብለው እንደገና ወሬያቸውን አቋረጡ፡፡
ወጣቱ አንዳች ነገር ጠረጠረ፡፡ አዛውንቱ የሆነ ማስረጃ ለማቅረብ እየሞከሩ እንደሆነና … ከጥንቱ ፈጣሪያቸው ጋር የነበራቸው መግባባትና ቅርርብ እንደገና እየናፈቃቸው እንደሆነ ጠረጠረ፡፡ ዝም ብሎ ማድመጡን ቀጠለ፡፡ በመሀል ቀስቃሽ ጥያቄዎችን ይሰነዝርላቸዋል፡፡
“እርስዎ የሚያምኑት ፈጣሪ፣ በምን ሀይማኖት ውስጥ የሚገኝ ነበር?”
“እምነት በመሰረቱ እንደ ባህል ከአፈራህ ማህበረሰብ የምትወርሰው ነው፣ መጀመሪያ፡፡ ዝግ ማህበረሰብ ውስጥ ያለ ፈጣሪና የሰለጠነ ወይንም ሰፊ አመለካከትን ያዳበረ ማህበረሰብ ያለው ፈጣሪ ይለያያል፡፡ … ግን መለያየቱ … ሔዶ የሚገናኝበት ቦታ ይኖረዋል፡፡ ሁሉም ፈጣሪን በሰው አምሳል … ወይንም ለሰው የተሳለ ማድረጋቸው ላይ ዞረው ዞረው ይግባባሉ፡፡ … ስለዚህ ፈጣሪ ራሱ የሚኖረው ገፅታ እንደ ሰው ገፅታ ከመሆን አይወጣም፡፡ ልክ ፈረንጅ ሰውና በአፍሪካ ጫካ ያለ የቡሽሜን ኋላ ቀር ሰው .. ሆነም ቀረ ሰው መሆናቸው ላይ እንደሚስማሙት ይሆናል፤ፈጣሪም … እና ምን ለማለት ፈልጌ ነው … ሰው ራሱን ከሰው በላይ አድርጎ ካልፈጠረ … ፈጣሪውም ከሰውኛ ባህርይ የተላቀቀ ሊሆን አይችልም፡፡”
“በእጅ አዙር የተነሳንበትን ጥያቄ መለሱልኝ። መፍጠር ያለብን ሰውን ነው ማለታቸው ነው፡፡ ሰውን አንድ ማድረግ እስካልተቻለ፣ፈጣሪም ይህንኑ የሚከተል ነው፡፡ …. ከባህላዊው እስከ ዘመናዊው …. ከጨካኙ እስከ ክርስቶሳዊው፣ ትሁት ፈጣሪ ያሉት ሀይማኖታዊ ትርክቶች … ስለ ፈጣሪ ከሚነግሩን ይልቅ ስለ ሰው ልዩነት የሚነግሩን መረጃ የበለጠ ነው፡፡”
“ስለ እድሜ ሊነግሩኝ የሚፈልጉት ነገር ነበር ልበል?” እያለ ወጣቱ በግድ መፅሐፉን አስጨበጣቸው፡፡ መቀበል የፈለጉ ግን አይመስሉም። … መፅሐፉ ውስጥ ያለውን አስተሳሰብ አልፈውት የሄዱ መሰለው፡፡ አልፈው ሄደው የት እንደደረሱ ግን እርግጠኛ አልነበረም፡፡ የደረሱበት ቦታ ከጠፋቸው ደግሞ አደገኛ ነው፡፡ በጠፋው መልስ ፋንታ ትዝታ በክፍተቱ መሀል ይገባል፡፡ የጥንቱ የፈጣሪ ዕምነት ከብዙ ጥንታዊ የልጅነት ትዝታ ጋር የተሳሰረ ስለሆነ ... ወጣትነቱን የሚመኝ ማንም ሰው … በወጣትነቱ ዘመን ያመልክ የነበረውን አምልኮ … ያፈቅራት የነበረችውን (አግብቶ ያስረጃትን) ኮረዳ መልሶ ለማግኘት ቢናፍቅ አይገርምም፡፡
ሰውዬውም ወደፊት ሄደው በስውር መስመር ወደ ጥንቱ ኋላቀርነታቸው እየተመለሱ መሰለው፤ ወጣቱ፡፡ እሱ ለማጣት እየተፍጨረጨረ ያለውን እምነቱን … ሽማግሌው መልሰው ለመጨበጥ እየተፍጨረጨሩ ነው፡፡ ግን ችግር አለው፡፡ ሰውዬው የሚታወቁት በተራማጅነታቸው ነው፡፡ ኋላቀር እምነትን በመሞገት ስማቸው የገነነ … ገናና መፅሐፍት አበርክተው ብዙውን ያነቁ ናቸው፡፡
መጀመሪያ ትዝታ ወደ ኋላ … ወደ ቀድሞው እምነታቸው እንዲመለሱ እንዳበረታታቸው ሁሉ … ይሉኝታ ደግሞ ወደ ኋላ መመለሻውን ዘግቶ አጠረባቸው፡፡ ወጣቱ ድንገት ሰውዬውን እየተመለከተ፣ይሄ ሁሉ የገቡበት አጣብቂኝ ወለል ብሎ ታየው፡፡ ተገለጠለት፡፡
ነገር ግን፤ ቢገለጥለትም፤ እሱ የሚወስደው ትምህርት የለም፤ከሰውዬው ተሞክሮ፡፡ እኔም ለመተው ወደፈለኩት እምነት አንድ ቀን ማጣፊያ ሲያጥረኝ መመለሴ አይቀርም ብሎ አላሰበም። ወጣት ነው፡፡ ዞሮ መግቢያው ቢታወቀውም ከመውጣት አያግደውም፡፡ ማመፅ አለበት፡፡ ለሁሉም ጊዜ አለው፡፡
“የልደት ቀኔ የሚያስታውሰኝ … ጊዜው የእኔ መሆኑን ነው” አላቸው፤ ለአዛውንቱ፡፡ የፈለገ ቢፈትጉትም ግን የሚሰጣቸው መፍትሄ አይኖርም። ወጣቱ ሽማግሌውን ወደ መተንኮስ ድንገት አመራ። በእሳቸው ሞት የእሱ ትንሳኤ ወይንም የእሱ ዘመን እንደሚጀምር አንዳች መገለጥ ሹክ ብሎታል፡፡
“ጊዜው የእኔ መሆኑንና መፅሐፉ ለእርሶ እንደማያገለግል ነው የልደቴ ቀን የገለጠልኝ … ይኼ አባባሌ የድፍረት አይሁንብኝና … በአባባሉ ከተስማሙ ለምን መፅሐፉን እንደ ልደት ቀን ስጦታ መርቀው አያበረክቱልኝም?!”
የንግግሩ ድፍረት በሽማግሌው ውስጥ የተሸሸገ ንዴት ቀሰቀሰ … ግን ንዴታቸው በማሸት ብዛት የጠቆረ አፍንጫቸውን በኃይል ከማቅላት በላይ ሌላ መፍትሄ ሊፈጥርላቸው አልቻለም፡፡ ጋቢያቸውን በመላጣው ጭንቅላታቸውና ሽበቶቻቸው ላይ አልብሰው ወጣቱን ትክ ብለው ብቻ መመልከት ቀጠሉ፡፡ “ምናልባት በመቃብሬ ላይ ነው እንጂ በህይወት ቆሜ አንተ የእኔን መፅሐፍ አትወስድም” እንደ ማለት ፍርጥም አሉ፡፡
“በእናንተ ትውልድ ባህል መሰረት … እድሜህን ባትገልጥልኝም … መልካም ልደት ተመኝቼልሀለሁ … መፅሀፍቶቼን ግን አልሰጥህም … የማልሰጥህ ደግሞ እኔ በሄድኩበት መንገድ እንድትጓዝ ስለማልሻ ነው፡፡ ቀስ ብለህ ኑር … ቀስ ብለህ አስብ፡፡ ቀስ ብለህ አስተውል፡፡ እና ለራስህ እምነት የሚመጥን ፈጣሪ ላይ ድረስ፡፡ መድረስ ባትችል እንኳን ወደ ኋላህ ተመልሰህ “ተሳስቼ ነበር” የማያስብልህን መንገድ ያዝ፡፡ በፍጥነት ቸኩሎ መውጣት ወደ ወጣህበት በስተርጅና የሚመልስህ ከሆነ፣ መሄድ የዜሮ ድምር ዋጋ ነው የሚኖረው … በሰዓቱ መጥተህ መፅሐፉን ስለመለስክልኝ ሳላመሰግንህ አላልፍም …” አሉና ወጣቱን አሰናበቱት፡፡ ወጣቱ የተናገሩትን አልሰማም፡፡ የሚጋልብ ደሙ ጆሮውን ደፍኖታል፡፡ ዋናው ፍላጎቱ ማንበብ ነው። ማንበብና አዛውንቱ ተጉዘው የደረሱበት ላይ ደርሶ ተስፋ አለመቁረጥ። የሽማግሌውን ስህተት በትኩስ ኃይልና ተስፋ ማደስ። መታደስ እንደሚችል እርግጠኛ ነበር። ሽማግሌው ገና ባይሞቱም በወጣቱ አይን ግን እንደ አስከሬን ተቆጥረዋል፡፡ ባይሞቱም ሞተዋል። ሐውልት ሊሆኑለት እንኳን አይችሉም። ከሽማግሌው የሚፈልገው ነገር መፅሐፎቻቸውን ብቻ ነበር፡፡ ምናልባት ሲሞቱ ያወርሱኝ ይሆናል የሚል የተስፋ ጭላንጭል በውስጡ ተቀጣጥሏል። መፅሐፍቱን ሊያወርሱት እንዲችሉ የስሜት ቀብድ በሰውዬው ውስጥ ማሳደር ይኖርበታል፡፡ ሰውየው የሀሳብ እንጂ የአካል ልጅ አላፈሩም፡፡ ምናልባት የአካል ልጅነትን ተውኔት ለራሱ ፅፎ እስኪሞቱ ቢጫወት መፅሐፍቱን ጥለውልን ይሞታሉ ብሎ በማሰብ የልደት ቀኑን አሳለፈው፡፡
… ከዚህ ባሻገር የልደት ትርጉም ለእሱ የተለየ ፍቺ አልነበረውም፡፡ እድሜው 25 ---- ደሙም የስሜት የደም ግልቢያ የፈጠነ ነበር፡፡ ሰክኖ ለማሰብ የሚያስፈልገው እድሜ ስንት እንደሆነ የማወቂያ አቅም አልነበረውም፡፡