Administrator
የከፍተኛ ትምህርት ኤግዚቢሽን በኮተቤ ዩኒቨርሲቲ ለ2 ቀናት ተካሄደ
• 7ሺ የሚደርሱ የዩኒቨርሲቲና የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ጎብኝተውታል
የአውሮፓ ህብረት ከኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው የ2017 ዓ.ም የአውሮፓ የከፍተኛ ትምህርት ኤግዚቢሽን፣ ባለፈው ሰኞ ህዳር 30 እና ታህሳስ 1 ቀን 2017 ዓ.ም በኮተቤ ዩኒቨርሲቲ የተካሄሰ ሲሆን፤ 7ሺ የሚደርሱ የሁለተኛ ደረጃና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንደጎበኙት አዘጋጆቹ ገለጹ፡፡
በኤግዚቢሽኑ መክፈቻ ላይ የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ አምባሳደር ሶፊ ፉሮም ኤምስበርገር፣ የኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ብርሃነ መስቀል ጠና፣ የአውሮፓ ህብረት አምባሳደሮችና ከፍተኛ የመንግሥት ሃላፊዎች ተገኝተው እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡
ለሁለት ቀናት በተካሄደው የከፍተኛ ትምህርት ኤግዚቢሽን፤ ቤልጂየም፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ ሀንጋሪ፣ስፔይንና ፖርቹጋልን ጨምሮ አስር የአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራትና ሦስት የአውሮፓ የትምህርትና ሥልጠና ተቋማት የሚሰጧቸን የከፍተኛ ትምህርት ዕድሎች ለጎብኚዎች አስተዋውቋል፡፡
የትምህርት ኤግዚቢሽኑ ዓላማ የአውሮፓ አባል አገራትና የከፍተኛ ትምህርት ተቋማቶቻቸው ለኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ያዘጋጇቸውንና የሚሰጧቸውን የነጻ ትምህርት ዕድሎች (ስኮላርሺፕ) ማስተዋወቅና ግንዛቤ መስጠት ነው ተብሏል፡፡ በዚህም ረገድ የዘንድሮ ኤግዚቢሽን የታለመለትን ግብ መምቱን አዘጋጆቹ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
የአውሮፓ የከፍተኛ ትምህርት በአውሮፓ ህብረት በአዲስ አበባ ሲዘጋጅ የዘንድሮ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን፤የመጀመሪያው ኤግዚቢሽን የዛሬ 5 ዓመት፣ በ2012 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል ነበር የተካሄደው፡፡
የአውሮፓ ህብረት፤ የኢትዮጵያን ትምህርት ከሚደግፉ የልማት አጋሮች ግንባር ቀደሙ ሲሆን፤በያዝነው የ2017 ዓ.ም ለ57 ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች ሙሉ የማስተርስ ዲግሪ የኤራስመብ ሙንደስ ነጻ የትምህርት ዕድል መስጠቱ ይታወቃል፡
የጃዋር መሃመድ “አልጸጸትም” በመጪው ሐሙስ ይመረቃል
የቀድሞው ታዋቂ አክቲቪስትና ፖለቲከኛ ጃዋር መሃመድ የጻፈው፣ “አልጸጸትም” የተሰኘ ግለ ታሪክ (Memoir) መጽሐፍ በመጪው ሳምንት ሐሙስ ታህሳስ 10 ቀን 2017 ዓ.ም፣ በኬንያ ናይሮቢ ይመረቃል፡፡ መጽሐፉ በአማርኛና ኦሮሚፋ ቋንቋዎች ነው የተዘጋጀው፡፡
ጃዋር ሞሃመድ የታዋቂው የኦሮምኛ አቀንቃኝ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያን ተከትሎ፣ ለእስር መዳረጉ የሚታወስ ሲሆን፤ ከእስር በተፈታ ማግስት ኢትዮጵያን ለቅቆ በመውጣት፣ መኖርያውን በኬንያ ናይሮቢ ማድረጉ ይታወቃል፡፡
“ተድባብ” ታሪካዊ ልብ-ወለድ መፅሐፍ ለገበያ ቀረበ
በአጭር ጊዜ ውስጥ በሥራዎቿ ተወዳጅነትን ባተረፈችው ደራሲ ህይወት ተፈራ የተፃፈው “ተድባብ” የተሰኘ ታሪካዊ ልብ ወለድ መፅሐፍ ከሰሞኑ ለገበያ ቀረበ። በዋልያ መፃሕፍት የታተመው ይህ ታሪካዊ ልብ-ወለድ፤ ጭብጡን በአድዋ ጦርነትና ድል ዙሪያ ያደረገ ነው፡፡
ደራሲዋ ከአንባቢያን ጋር ለመጀመሪያ ጊዜ የተዋወቀችው “ማማ በሰማይ” በሚል ወደ አማርኛ በተተረጎመው “Tower in the sky” በተሰኘ የበኩር መጽሐፏ ነው፡፡ ለጥቃም “ሃሰሳ” በሚል የተተረጎመ “Mine twin” እና “ምንትዋብ” የተሰኙ ታሪካዊ ልብወለዶችን ለአንባቢያን አድርሳለች፡፡ ከሰሞኑ ለንባብ የበቃው “ተድባብ” ታሪካዊ ልብ ወለድ ለደራሲዋ አራተኛ ሥራዋ መሆኑ ነው።
“ተድባብ” ለደራሲ ህይወት ተፈራ አራተኛ ሥራዋ ነው
ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳንና ታንዛኒያ የኤሌክትሪክ ኃይል ልትሸጥ ነው
ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳንና ታንዛኒያ የኤሌክትሪክ ኃይል ለመሸጥ በዝግጅት ላይ መሆኗን የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትር አቶ ሀብታሙ ኢተፋ ትናንት ማምሻውን አስታውቀዋል።
ኢትዮጵያ ላለፉት ዓመታት ለሱዳን፣ኬንያና ጅቡቲ የኤሌክትሪክ ኃይል ስትሸጥ የቆየች ሲሆን፤ አሁን ደግሞ ለደቡብ ሱዳንና ታንዛኒያ ለመሸጥ በዝግጅት ላይ መሆኗ ተነግሯል፡፡
ኢትዮጵያ፣ ኬንያንና ታንዛኒያን የሚያገናኘውን 400 ኪሎ ዋት የኤሌክትሪክ ማስተላለፊያ መስመር በቅርቡ ባጠናቀቀችው ኬንያ በኩል፣ ኢትዮጵያ ለታንዛኒያ የኤሌክትሪክ ኃይል እንደምታቀርብ ይጠበቃል፡፡
የምስራቅ አፍሪካ ፓወር ፑል (ኢኤፒፒ) ስብሰባ ከትናንት ጀምሮ በኬንያ ሞምባሳ እየተካሄደ ሲሆን፤ የኢትዮጵያ ተወካይ የኃይል አቅርቦቱን ስምምነት ለማጠናቀቅ ከታንዛኒያና ኬንያ አቻዎቻቸው ጋር እየተወያዩ መሆኑ ታውቋል፡፡
ኢኤፒፒ በምስራቅ አፍሪካ በሚገኙ 11 ሀገራት የኤሌክትሪክ ሃይሎቻቸውን ለማገናኘት የተቋቋመ ሲሆን፤ ብሩንዲ፣ የኮንጎ ዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ፣ ግብፅ፣ ኢትዮጵያ፣ ኬንያ፣ ሩዋንዳ፣ ሱዳን፣ ታንዛኒያ፣ ሊቢያ፣ ጅቡቲና ኡጋንዳ የኢኤፒፒ አባል ናቸው።
አማራ ባንክ አጠቃላይ ሃብቱ ከ35 ቢ. ብር መላቁን አስታወቀ
አማራ ባንክ የባለ አክስዮኖች 3ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን በዛሬው ዕለት በሚሊኒየም አዳራሽ ያካሄደ ሲሆን፤ የባንኩ አጠቃላይ ሀብት 35.2 ቢሊዮን ብር መድረሱን አስታውቋል፡፡
አማራ ባንክ ባለፉት ዓመታት ተግዳሮቶች ቢገጥሙትም፣ ዘንድሮ 669 ሚሊዮን ብር ትርፍ ማግኘቱን ይፋ አድርጓል፡፡
ባንኩ ለደንበኞቹ የሚሰጠውን የብድር መጠን 33 በመቶ በማሳደግ 20 ቢሊዮን ብር ገደማ ማድረሱን ያስታወቀ ሲሆን፤ አጠቃላይ የተቀማጭ ገንዘብ መጠኑ 26 በመቶ አድጓል፡፡ የመደበኛና ከወለድ ነፃ የባንክ አገልግሎት በድምሩ 25 ቢሊዮን ብር መድረሱንም አመልክቷል፡፡
በተጨማሪም የባንኩ ዓመታዊ ገቢ 146 በመቶ ዕድገት በማሳየት፣ 4.4 ቢሊዮን ብር ገቢ አስመዝግቧል።
ከ1.8 ሚሊዮን በላይ ደንበኞችና ወደ 600 ሺ የሚጠጉ የሞባይል ባንኪንግ ተጠቃሚዎች ያሉት አማራ ባንክ፤ የደንበኞቹ ብዛት እያደገ መምጣቱን አስታውቋል።
በተደራሽነት ረገድም በበጀት አመቱ 143 አዳዲስ ቅርንጫፎችን በመላ አገሪቱ በመክፈት አመርቂ እድገት ያስመዘገበ ሲሆን፤ አጠቃላይ የቅርንጫፎቹን ቁጥርም 310 አድርሷል፡፡
”አዲስ ገና 2017 ኤክስፖ“ የፊታችን አርብ ይከፈታል
• ኤክስፖው በኤግዚቢሽን ማዕከልና በመስቀል አደባባይ ይካሄዳል
• አዘጋጁ ጨረታውን ያሸነፈው በ80ሚ.600ሺ ብር ነው
• መኖሪያ ቤት የሚያሸልም የሎተሪ ዕጣ ተዘጋጅቷል
ሮበስት ቢዝነስ ግሩፕና ሠላሳ መልቲ ሚዲያ ከንግድና ቀጠናዊ ትስስር ሚኒስቴር ጋር በመተባበር ያዘጋጁት ”አዲስ ገና 2017 ኤክስፖ“፤ የፊታችን አርብ ታሕሳስ 4 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከልና በመስቀል አደባባይ ይከፈታል፡፡
የገና ኤክስፖን በተመለከተ አዘጋጆቹ በዛሬው ዕለት ረፋዱ ላይ በስካይላይት ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
በመግለጫው ላይ እንደተነገረው፤ የዘንድሮው የገና ኤክስፖ ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከልና በመስቀል አደባባይ በጥምረት ይካሄዳል፡፡
በገና ኤክስፖው ላይ ከ500 በላይ የሚሆኑ የአገር ውስጥ አምራች ፋብሪካዎች፣ የኢንዱስትሪ መንደሮች፣ ትላልቅ አስመጪዎች፣ ማህበራትና ዩኒዬኖች፣ የሪል እስቴት አልሚዎች፣ የፋይናንስ ተቋማት፣ የኤሌክትሪክ መኪና አቅራቢዎችና ከስምንት የተለያዩ አገራት የተውጣጡ የውጭ ኩባንያዎች ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡
የበዓል ኤግዚቢሽኖች የሚዘጋጁበት አንዱ ዓላማ ገበያውን ለማረጋገት እንደሆነ ያስረዱት አዘጋጆቹ፤ በአንድ የ20 ሊትር ዘይት ላይ እስከ 400 ብር ቅናሽ ተደርጎ ለሸማቹ እንደሚቀርብ ጠቁመዋል፡፡ ሌሎች የዕለት ተዕለት ፍጆታዎችም በፋብሪካ ዋጋ ለሽያጭ እንደሚቀርቡ ተነግሯል፡፡
እስከ ታሕሳስ 28 ቀን 2017 ዓ.ም ለ25 ቀናት ክፍት ሆኖ በሚዘልቀው የገና ኤክስፖ የተለያዩ መዝናኛዎች እንደሚኖሩ የተገለጸ ሲሆን፤ 100 ተወዳጅ ድምጻውያን ከአምስት የሙዚቃ ባንዶች ጋር ታዳሚዎችን እንደሚያዝናኑ ታውቋል፡፡
የተለያዩ የህጻናት መጫዎቻዎችን ያካተተ “የህጻናት ዓለም” መዘጋጀቱም በመግለጫው ላይ ተጠቁሟል፡፡ ለልጆች በተዘጋጀው የጌም ዞን፤ የዳይኖሰሮች ትርኢት፣ የግመልና ፈረስ ሽርሽር፣ የገና ጨዋታና የህጻናት የገና ስጦታዎች እንደሚኖሩም ታውቋል፡፡
በዚህ ኤክስፖ ላይ የፌስቲቫል ድባብ ለመፍጠር የተለያዩ ጥረቶች መደረጋቸውንም አዘጋጆቹ አብራርተዋል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዱ ትልቁ የገና ዛፍ ሲሆን፤ ሌላው 2017 ስኒዎችን የሚይዝ ትልቅ ረከቦት ነው ተብሏል፡፡
”አዲስ ገና 2017 ኤክስፖ“ን ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ህዝብ ይጎበኘዋል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፤ የመግቢያው ዋጋ 100 ብር እና 200 ብር መሆኑን አዘጋጆቹ ተናግረዋል፡፡
በዘንድሮው የገና ኤክስፖ ከብሔራዊ ሎተሪ አስተዳደር ጋር በመተባበር የመኖሪያ ቤት የሚያሸልም የሎተሪ ዕጣ መዘጋጀቱም ታውቋል፡፡
ሮበስት ቢዝነስ ግሩፕ የአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ለገና በዓል ያወጣውን ጨረታ ያሸነፈው በ80 ሚሊዮን 600 ሺ ብር ሲሆን፤ ይህም በማዕከሉ ታሪክ ከፍተኛው የጨረታ ዋጋ መሆኑ ታውቋል፡፡
የአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል ሃላፊዎች በመግለጫው ላይ በሰጡት ማብራሪያ፤ ማዕከሉ ለገና በዓል ባወጣው ግልጽ ጨረታ ከ5 በላይ ተወዳዳሪዎች የተሳተፉ ሲሆን፤ በመጨረሻም ሮበስት ቢዝነስ ግሩፕ ጨረታውን በከፍተኛ ዋጋ አሸንፏል፡፡
“አንድም ከቀበሮ፤ አንድም ከአንበሳ ተማር” አንበሳ ከወጥመድ ለማምለጥ አይችልም። ቀበሮ ደግሞ ከተኩላ ለማምለጥ አትችልም። ወጥመዱን ለማየት ቀበሮ ሁን። ተኩላ እንዳይጠጋህ አንበሳ ሁን።
ማኪያቬሊ (ጣሊያናዊ የታሪክ ባለሙያ፣ የሀገር መሪ፣ እና የፖለቲካ ፍልስፍና አዋቂ)
አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ።
የዱር አራዊት ንጉሥ አንበሳ ታሞ አልጋ ላይ ዋለ። ጠያቂና አስታማሚ አጣ። ከህመሙም በላይ ጠያቂ ማጣቱ በጠናበት ጊዜ፣ ለአሣማና ለዶሮ በደብዳቤ መልዕክት ላከ። እንዲህ ብሎ፡-
“ውድ አሳማ!
ውዲት ዶሮ!
እነሆ ካመመኝና አልጋ ከዋልኩ አያሌ ወራት ሆኑኝ። እህል ከቀመስኩ ደግሞ ሣምንት አለፈኝ። ዞር ዞር ብዬ የሚበላ ፈልጌ እንኳ አፌ እንዳላረግ ህመምተኛ ሆንኩ። አቅሜም ደከመ። የሰው ልጆች አንበሳ ሲያረጅ የዝምብ መጫወቻ ይሆናል፤ የሚሉት የዋዛ አነጋገር አይደለም። ዱሮ የሚሰግዱልኝ፣ የሚሽቆጠቆጡልኝና ከሥሬም የማይጠፉ ብዙ አውሬዎች ዛሬ አንዳቸውም አጠገቤ ያሉ አይመስሉም። አንዳንዱ ያለወትሮው ዝምተኛ ሆኗል። በአንፃሩ አንዳንዱ፣ ምንም ፍሬ ጠብ አይለውም እንጂ፤ አፍ ለቆበታል። አንዳንዱ እኔ ካልኖርኩ የማይኖር ይመስል በፍርሃት ተውጦ ተደብቆ ይተኛል። ሌላ ቀርቶ፣ አይምሬውን ክርኔን የቀመሱት፣ ሳገሣ ድራሻቸው ይጠፋ የነበሩት እነ አያ ጅቦ፣ እነ አያ ከርከሮ፣ እነ ብልጢት ጦጣ፣ ዛሬ አልጋዬ ድረስ መጥተው እንኳ ለመጠየቅ ንቀት አደረባቸው። እንዲያውም “አንበሳ ከታመመ፣ የልብ ወዳጅ ከጠመመ፣ መመለሻ የለውም” እያሉ እየረገጡ አላገጡብኝ አሉ። በዙሪያዬ የነበሩት ሁሉ “አምላክ አንተንም እኛንም እኩል ነው የፈጠረን” ማለት ጀምረዋል። ይሄ ቀን የማያልፍና፣ ከታመምኩት በሽታ ድኜ፣ ካልጋ ቀና የማልል መስሏቸው ነው። እንግዲህ የቀራችሁኝ ውድ ወዳጆች እናንተና ይህን ደብዳቤ ይዞላችሁ የመጣው ዝንጀሮ ብቻ ናችሁ። ስለዚህ አደራ ሳልሞትባችሁ ድረሱልኝ።”
ፊርማ የማይነበብ
የናንተው አንበሳ፣
የጥንቱ የጠዋቱ የዱር አራዊት ንጉሥ
አሳማና ዶሮ ደብዳቤው እንደደረሳቸው በጣም አዘኑ።
“ምን ብናደርግለት ይሻላል?” አለ አሳማ።
ዶሮም፤ “መቼም ነግ በእኔ ማለት ደግ ነው። አንድ ነገር ማድረግ አለብን”
አሳማ፤ “ግን አያ አንበሶን እንዲህ እስኪማረር ድረስ ያደረሱት እነማን ይሆኑ?”
ዶሮ፤ “ዛሬ ማን ይታመናል ብለህ ነው አሳምዬ? የልብ ወዳጅ የታለና? ያው እሱ ራሱ የጠቃቀሳቸው በጣም ቅርብ ቅርብ ያሉ ባለሟሎች እነ አያ ጅቦ፣ እነ እመት አህያ፣ እነ አቶ በቀቀን፣ እነ ጆሮ-ትላልቄ ይሆናሏ።”
አሳማ፤ “አትይኝም? ጆሮ.. ትላልቄም ጨከነበት?”
ዶሮ፤ “እየነገርኩህ! ባለንበት ዘመን፣ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር ማንም አይተኛም”
አሣማ፤ “ዕውነትሽን ነው። በይ እኛም ሳይረፍድ የምንይዘውን ይዘን ሄደን እንጠይቀውና ይውጣልን”
ዶሮ፤ “እንዲህ እናድርግ። እኔ እንቁላል ላዋጣ። አንተ ደግሞ ስጋ አዋጣና ሃምበርገር ይዘንለት እንሂድ”
አሣማ፤ “በጣም ድንቅ ሃሳብ አመጣሽ። በቃ ሀምበርገር እንውሰድለት”
በዚሁ ተግባቡና ጠዋት ወደ አንበሳው ሊሄዱ ተስማምተው ተለያዩ።
ጥቂት እልፍ እንዳሉ ግን፤ አሣማ አንድ ነገር ትዝ አለውና ዶሮዋን ጠራት። ከዚያም “ስሚ አንቺ ዶሮ፤ አሁን እናዋጣ የተባባልነው፤ ሚዛናዊ መዋጮ አይደለም። እኔ ተበድያለሁ!”
ዶሮም ነገሩ ስላልገባት፤ “ለምን? እንዴት ነው ሚዛናዊ ያልሆነው?”
አሳማም፤ “አየሽ፤ አንቺ ዕንቁላሉን የምታዋጪው ወልደሽው ነው። እኔ ግን ሥጋ እምሰጠው ከገዛ አካሌ ቆርጬ ነው። ያንቺ ተሳትፎ ብቻ ነው (Participation እንዲሉ)። የእኔ ግን ጉዳዩ ውስጥ በአካል መግባት ነው (Involvment እንዲሉ)” አላት።
***
ህመም፣ ችግርና ሣንካ ሲያጋጥመን ወዳጅ አይክዳ። እንደ አረጀ አንበሳም የዝምብ መጫወቻ ከመሆን ይሰውረን። ከፍሬ-ቢስ ልፈፋ ያውጣን። በእኩልነት የማያምን “ዲሞክራት መሪ” አያጋጥመን።
በአገራችን ውስጥ ያሉ የፖለቲካ ሰዎች ሚና፣ ጉዳዩ ውስጥ የመግባት እንጂ ዕንቁላል የመጣል ተሳትፎ ብቻ እንዳይሆን የሁሉም ወገን ጥረትና ትግል ሊኖርበት ይገባል። በሀገራችን የፖለቲካ ውጣ - ውረድ ውስጥ አያሌ አንበሶች ታይተዋል። ሆኖም የአንበሳነታቸው መጠንም ሆነ አንበሳዊ ባህሪያቸው፤ የተለያየ ሆኖ እናገኘዋለን። አንዳንዱ በጭራሽ ሌላ ፍጡር አያስጠጋም። ንፁህ ነው እንኳ ቢባል። ዲ.ኤች.ሎረንስ እንዳለው ነው፡- “አንበሳን ማንም ኃይል፤ ከበግ ግልገል ጋር ሊያስተኛው አይችልም። ግልገሏ ሆዱ ውስጥ ካልገባች በስተቀር።” አንዳንዱ ደግሞ ቀን ሲጨልምበት ወይም እክል ገጥሞት ከአልጋ ሲውል በቀላሉ የሚደፈር ይሆናል። ሆራስ የተባለው የዜማና ምፀታዊ ግጥም ፀሀፊና ታዋቂ ሮማዊ (ከክርስቶስ ልደት በፊት በ65-ዓመት)፤
ታሞ ልትጠይቀው፣ ሄዳ ወደ አንበሳ
ቀን- አይታ ቀበሮ፣ ነገር ልታነሳ
እንደዚህ አለችው፣ በሰላ ወቀሳ
“ጌታው አቶ አንበሶ፤
የእግር-ጥፍር አሻራህ፣ ያስፈራኛል በጣም፤
ግን ምስሉ ይገርማል፤ መሬት ላይ ሲታተም
ወደ ራስህ ዞሮ፣ አንተኑ ሲጠቁም።
ከያዘው አቅጣጫ እንደማይመለስ፣ አሳምሬ ባቅም
የእግር- ጥፍር አሻራህ፣ ያስፈራኛል በጣም።
ከሄደበት መንገድ፣ ወደኔ ባይመጣም።”
ብሎ እንደፃፈው ነው።
አንዳንዶቹ፤ በ19ኛው ክ/ዘመን አጋማሽ የነበሩት የአርጀንቲናው ፕሬዚዳንት በአንድ ወቅት “በአሁኑ ሰዓት ሰላማዊ አብዮተኛ (Pacifist Revolutionary ማለት) አትክልት-በል አንበሳ Vegetarian Lion ማለት ነው” ብለው እንደገለጹት ዓይነት ናቸው።
በአገሬው ዐይን ሌላ፣ በአለም አቀፍ ማህበረሰብ ዐይን ሌላ፣ የሆኑም አሉ። ሩሲያዊው ደራሲ ሶልዘንስቲን እንደሚለው፤ “ለእኛ ሩሲያ ውስጥ ላለነው፤ ኮሙኒዝም የሞተ ውሻ እንደማለት ነው። ለብዙ ምዕራባውያን ግን በህይወት ያለ አንበሳ ይመስላቸዋል” ማለት መሆኑ ነው።
ሌሎች አንበሶች ደግሞ፤ ዊንስተን ቸርችል 80ኛውን የልደት በዓላቸውን ሲያከብሩ ለሁለቱም ምክር ቤቶች እንደተናገሩት፤ “አገሬ የአንበሳ ልብ አላት። እኔ ደግሞ እንደዳልጋ አንበሳ መጮህን ታድያለሁ”፤ የሚሉ ናቸው።
በኢትዮጵያ የፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ውስጥ ሁሉ ያየናቸው የፖለቲካ ፓርቲም ሆነ የብዙኃን ንቅናቄ መሪዎች አንድ የጋራ ጠባይ አላቸው። ይህንን ፀባይ አፍሪካዊው የስዋሂሊኛ ተረት በደንብ ይገልጠዋል፡- “የተቆለመመ ጥፍር ያላቸው ሁሉ አንበሳ አይደሉም”።
ትላንት በተካሄደውም ሆነ ዛሬ በአገራችን እየተካሄደ ባለው ፖለቲካዊ ሂደት ውስጥ የሚጓዙ ኃይሎች ሁሉ መማርና ማወቅ ያለባቸው አንድ ቁም ነገር አለ፡-
“አንድም ከቀበሮ፤ አንድ ከአንበሳ ተማር”
አንበሳ ከወጥመድ ለማምለጥ አይችልም።
ቀበሮ ደግሞ ከተኩላ ለማምለጥ አትችልም።
ወጥመዱን ለማየት ቀበሮ ሁን።
ተኩላ እንዳይጠጋህ አንበሳ ሁን።
ኢህአፓ የገዢው ፓርቲ የ5 ዓመት ጉዞ ኪሳራ ነው አለ
ባለፉት አምስት ዓመታት ገዢው ፓርቲ ተገምግሞ ከስሯል ሲሉ የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበር መጋቢ ብሉይ አብርሃም ሃይማኖት ተናገሩ።
መጋቢ ብሉይ አብርሃም ሃይማኖት ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ የብልጽግና ፓርቲ የአምስት ዓመታት ጉዞ ሲገመገም፣ የህግ የበላይነትን በማስከበርና ኢኮኖሚውን በማሳደግ በኩል ድክመት ማሳየቱን ገልፀዋል። “ከኮሪደር ልማትና ከሚያብለጨልጩ ነገሮች ውጪ ለሕዝባችን ጠብ የሚል አዲስ የኢኮኖሚ ለውጥ አልታየም” ሲሉም ተችተዋል።
በከፍተኛ የዋጋ ንረት ሳቢያ፣ ዜጎች የዕለት ጉርሳቸውን ማግኘት አለመቻላቸውን የሚገልፁት የኢህአፓ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀመንበር፤ በጥቅሉ አሁን ላይ ያለው ወጣት ተስፋ መቁረጡን ይናገራሉ።
የጸጥታና ሰላም ጉዳይን በተመለከተ የሕግ የበላይነት አለመከበሩን የጠቆሙት መጋቢ ብሉይ፤ “ሕገ መንግስታዊ መብቶች ጭምር እየተናዱ ነው።” ብለዋል። በመንግስትነት የሚያስተዳድረው ብልጽግና ፓርቲ፤ ሕገ መንግስቱን አክብሮ ማስከበር ሲገባው፣ እሱም አላከበረውም፤ ማስከበርም አልቻለም” ሲሉም ነቅፈዋል።” በተጨማሪም፣ ፓርቲው አገራዊ ችግሮችን ለመቅረፍ የሚጠቀመው ብቸኛ አማራጭ ጦርነት ብቻ ነው። ሲሉም ትችታቸውን ሰንዝረዋል።
“ብልጽግና ፓርቲ በጉልበት እንጂ በፖለቲካዊ ውይይትና ንግግሮች መፍትሔ ለማምጣት ሲንቀሳቀስ አልታየም። ከብዙ ዕልቂት በኋላ፣ የተወሰነ ነገር ይጀምርና በሁሉም ቦታ ላይ ተግባራዊ ስለማይሆን በአንድ ቦታ ግጭት ጋብ ሲል፣ በሌላ ቦታ እንደገና ያገረሻል።” ይላሉ፣ መጋቢ ብሉይ አብርሃም።
ባለፉት አምስት ዓመታት ውስጥ ገዢው ፓርቲ ተገምግሞ ከስሯል ያሉት የኢሕአፓ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበር፤ ጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ባለፈው ቅዳሜ፣ በዓድዋ መታሰቢያ ሙዚየም በተካሄደው የብልጽግና ፓርቲ አምስተኛ ዓመት የምስረታ በዓል የማጠቃለያ ፕሮግራም ላይ ለተፋላሚዎቻቸው “ሺህ ዓመት ቢታገሉንም አያሸንፉንም” ሲሉ መናገራቸው ጦርነት እንደሚፈልጉና በተቃራኒ ጎራ የሚገኙ ለሺህ ዓመት ትግል እንዲያካሂዱ ምክረ ሃሳብ እንደሰጡ የሚያስቆጥርባቸው ነው ብለዋል።
“ከአንድ አገር የሚመራ ፓርቲ ይህ ንግግር አይጠበቅም። ጉልበትና አቅሙ ቢኖረውም እንኳ፣ ችግሮችን በሰላም እንዲፈቱ ነው ማድረግ ያለበት፤ ምክንያቱም የአገር ውስጥ ችግሮች ተባብሰው ውስጣዊ አንድነት ከሌለ፣ ለጠላት በሮች ክፍት ይሆናሉ። አገርም ለከፍተኛ አደጋ ትጋለጣለች።” ብለዋል፣ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበሩ። “ጠቅላይ ሚኒስትሩ ፖለቲካዊ ጥያቄዎች በውይይትና ድርድር መፈታት እንደሚችሉ ነው መናገር የነበረባቸው” ብለዋል።
በሚቀጥለው ዓመት ብሔራዊ ምርጫ የሚደረግ ቢሆንም፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች ግጭቶች በመከሰታቸው ሳቢያ የፓርቲያቸው እንቅስቃሴ መገደቡን የተናገሩት መጋቢ ብሉይ አብርሃም፤ በተለይ፣ በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች ማደራጀትና እንቅስቃሴ ማድረግ እንዳልተቻለ ገልፀዋል።
በአዲስ አበባ ከተማም ፓርቲያቸው በመንግስት በሚደርስበት ጫና ሳቢያ ጠቅላላ ጉባዔውን ለማድረግ አለመቻሉን የጠቆሙት መጋቢ ብሉይ አብርሃም፤ የፖለቲካው ምህዳር መጥበቡን የሚያሳዩ ከበቂ በላይ አብነቶች መጥቀስ ይቻላል ብለዋል።
ገዢው ፓርቲ ያለፉትን አምስት ዓመታት በጥልቀት ገምግሞ ከስሕተቶቹ በመማር ከቻለ አሁን የሚታየውን ችግር እንዲቀርፍ ያሳሰቡት ፖለቲከኛው፤ ሁሉንም ችግር በጉልበት ለመፍታት ከማሰብ ይልቅ በፖለቲካዊ መፍትሔዎች ላይ ማተኮር እንደሚያስፈልግ መክረዋል። “ለሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴዎች ምቹ ምህዳር መፍጠርና ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን ማስፋት ብልጽግና ፓርቲ የሚሰጠን ልዩ ስጦታ አይደለም፤ መብታችን ነው” የሚሉት ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበሩ፣ “ኢትዮጵያ አሁን እየሄደችበት ባለው መንገድ ከቀጠለች፣ የመፍረስ አደጋ ይጋረጥባታል” ብለዋል።
“በአሁኑ ወቅት በስቃይና በመከራ ላይ የሚገኘው ሕዝብ ብሶቱን ሲያቀርብ አለመናቅና ዝቅ ብሎ ማዳመጥ እንጂ በተለያየ መንገድ ለመሸወድ መሞከር ጥሩ ውጤት አያመጣም። “ያሉት የኢህአፓ አመራሩ፤” ችግሩ በፍጥነት መፍትሄ ካልተበጀለት እየሰፋ ሄዶ ብልጽግና ፓርቲንም ጭምር ሰለባ የሚያደርግ ቀውስ ሊፈጠር ይችላል”ሲሉ አሳስበዋል።
የመምህራን ማሕበሩ በማህበራዊ ሚዲያ የሥራ ማቆም አድማ መጠራቱን አላወቅም አለ
“በሥራ ማቆም አድማው የሚጎዳው አገርና ትውልድ ነው”
በተለያዩ የማህበራዊ ትስስር ገጾች በመላ አገሪቱ የሚገኙ መምህራን ከታሕሳስ 1 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ የስራ ማቆም አድማ እንዲያደርጉ የተሰራጨውን ጥሪ እንደማያውቅ የኢትዮጵያ መምሕራን ማሕበር አስታወቀ። “ወቅቱን ያገናዘበ የደመወዝ ጭማሪ ይከፈለን” በሚል የሥራ ማቆም አድማው በማህበራዊ ሚዲያ መጠራቱን ለማወቅ ተችሏል።
የኢትዮጵያ መምህራን ማሕበር ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ሽመልስ አበበ ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ፤ ከሰሞኑ ብቻ ሳይሆን በየጊዜው የሥራ ማቆም አድማ እንዲደረግ የተለያዩ ጥሪዎች እንደሚቀርቡ ጠቁመው፣ አሁን የተጠራውን የስራ ማቆም አድማ ግን ማህበራቸው እንደማያውቀው ገልፀዋል።
የደመወዝ አለመከፈል፣ የደሞዝ መቆረጥ፣ የመምህራን እስርና የመሳሰሉት ችግሮችን ዕልባት ለመስጠት ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር እየተነጋገሩ መሆኑን የገለጹት የማህበሩ መሪ፤ ባለፈው ጥቅምት ወር በአዳማ ከተማ የማህበሩ ምክር ቤት ባካሄደው ስብሰባ ላይ የመንግሥት አካላት ተገኝተው፣ በመምህራን የሚቀርቡ ቅሬታዎችን እንዲያውቁ መደረጉን ተናግረዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ፣በዚሁ ስብሰባ ላይ በጉልህ የተነሱ ሃሳቦችን በውሳኔ ሃሳብና በአቋም መግለጫ መልክ በማጠናቀር፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤትን ጨምሮ ወደ 11 ገደማ ለሚሆኑ የፌደራል መስሪያ ቤቶች እንዲሁም መላኩንም ጠቁመዋል፡፡
አያይዘውም ፤የደረጃ ዕድገትና የትምሕርት ማሻሻያ፣ ውዝፍ ክፍያዎችን፣ እንዲሁም የሁለትና ሦስት ወር ደመወዝ ያልከፈሉ አካባቢዎች የትኞቹ እንደሆኑ ለማጣራት የመረጃ ማሰባሰብ ስራ እየተሰራ እንደሚገኝ ምክትል ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል። በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች የደመወዝ አከፋፈል ላይ ችግሮች እንደሚስተዋሉ የጠቆሙት ምክትል ፕሬዚዳንቱ፤በተለያዩ ምክንያቶች የመምህራን ደመወዝ እንደሚቆረጥም ገልፀዋል።
“ለመምህራኑ ደመወዝ መቆረጥ እንደ ምክንያት የሚቀርበው ደግሞ ‘ለልማት’ የሚል ነው” ያሉት አቶ ሽመልስ፤ በዚያ ላይ መምህራን ደመወዛቸው እንዲቆረጥ ፈቃደኛ መሆናቸው አይጠየቅም” ብለዋል። “የደመወዛቸውን መቆረጥ ተከትሎ የመማር ማስተማር ሂደቱ ይስተጓጎላል። ምክንያቱም መምህራኑ መብታቸውን ለማስከበር የተለያዩ እንቅስቃሴዎችን ያደርጋሉ” ሲሉ አስረድተዋል። እነዚህን እንቅስቃሴዎች በማረጋጋት፣ መምህራን ስራቸውን እንዲሰሩ ከማስቻል ባሻገር፣ ማሕበሩ የመንግስት አካላት፣ ያለመምህራን ፈቃደኝነት ደመወዝ ከመቁረጥ እንዲታቀቡ ለማድረግ እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል።
ለአብነት ያህል በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ ኮሬ ዞን፣ ሳርማሎ ወረዳ ከመምህራን ደመወዝ 25 በመቶ መቆረጡን ተከትሎ የወረዳው ባለስልጣናት ጥያቄ ያነሱ 66 መምህራንን በጸጥታ ሃይሎች አማካይነት ሕዳር 11 እና 12 ቀን 2017 ዓ.ም. በቁጥጥር ስር እንዲውሉ ማድረጋቸውን አቶ ሽመልስ ያወሳሉ። ማህበሩ የእነዚህ መምህራን ጉዳይ መረጃው እንደደረሰው፣ ከሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ጋር በመነጋገር፣ እንዲሁም የማሕበሩ ተወካዮችና የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች ቦታው ድረስ በመገኘት የታሰሩት መምህራን ከእስር እንዲፈቱ ለማድረግ መቻሉን ተናግረዋል።
በሌላ በኩል፣ የዩኒቨርስቲ መምህራን “የፌደራል ተቋም ሰራተኞች ናችሁ” ተብለው የቤት መስሪያ ቦታ በሚሰጥበት የመኖሪያ ቤት ፓኬጅ ተጠቃሚ አለመሆናቸውን ያነሱት ምክትል ፕሬዚዳንቱ፤ ማሕበራቸው አገልግሎቱ ለዩኒቨርስቲ መምህራኑ መሰጠት እንዳለበት በማሳሰብ፣ ለሚመለከታቸው የመንግስት አካላት ደብዳቤ እንደጻፈ ገልጸዋል። ከትርፍ ሰዓት ሥራ ጋር በተገናኘም ጥያቄዎች እንደሚነሱ አቶ ሽመልስ ጠቅሰዋል፡፡
“የዩኒቨርስቲ መምህራን ‘ደብል ታክሴሽን (Double Taxation) እየተተገበረብን ነው’ ይላሉ። በመጀመሪያ መደበኛ ደመወዛቸው ታክስ ይደረጋል። የትርፍ ሰዓት ስራ ሲሰሩ ደግሞ፣ በዚያው ስራ ያገኙት ክፍያ ታስቦ በተጨማሪነት ታክስ ይደረግባቸዋል። በዚህም ምክንያት ደመወዛቸው ተቆራርጦ ለመምህራኑ የሚደርሳቸው ገቢ እዚህ ግባ የሚባል አይደለም። አብዛኛው ለታክስ የሚውል ነው።” በማለት ያስረዳሉ፤ አቶ ሽመልስ። ማሕበራቸው ይህ የታክስ አሰራር ትክክል አለመሆኑን ተገንዝቦ አቋም እንደወሰደበትም ጠቁመዋል።
“ከመምህራን እኩል እየወጣን እየወረድን ችግሮችን ለመፍታት በመንቀሳቀስ ላይ ነን” ያሉት የማሕበሩ ምክትል ፕሬዚዳንት፤ “በማሕበራዊ ሚዲያ ላይ እየተላለፈ ባለው የስራ ማቆም አድማ ጥሪ የሚጎዳው አገርና ትውልድ ነው።” ብለዋል። “መምህራን ሥራ አቁመው ወደዚህ ያልተገባ ተግባር ይገባሉ ብዬ አላስብም” ሲሉም ግምታቸውን ገልፀዋል።
ከሰሞኑ በማሕበራዊ ትስስር ገጾች ላይ የተጠራውን የመምህራን የሥራ ማቆም አድማ ማሕበራቸው እንደማያውቀውም አቶ ሽመልስ አክለው ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
በትግራይ የግሪሳ ወፍ መንጋ በብዛት መከሰቱ ተገለጸ
ብዛታቸው ከ4-5 ሚሊዮን ይደርሳሉ ተብሏል
በትግራይ ክልል የግሪሳ ወፍ መንጋ በብዛት መከሰቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ የገለጸ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት ብዛታቸው ከ4-5 ሚሊዮን እንደሚደርሱ አመልክቷል፡፡ የቢሮው የሕዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ሚኪኤለ ምሩጽ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፤ ግሪሳ ወፍ በአጎራባች ክልሎች እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን፣ የግብርና ሚኒስቴር የመከላከል ስራዎችን እንደሚሰራ ስለሚገመት በትግራይ ከፍተኛ ችግር ይፈጥራል የሚል ግምት አልነበረም ብለዋል። ይሁንና ባለፈው ሳምንት የግሪሳ ወፍ መንጋ በድንገት ወደ ትግራይ ክልል መግባቱን ሃላፊው ገልፀዋል።
“የግሪሳ ወፍ መንጋው መጀመሪያ የገባው በራያ ጨርጨር ወረዳ በኩል ነው” ያሉት አቶ ሚኪኤለ፤ በወረዳው ባጌ ደልቦ በሚባል አካባቢ በሚገኙ የሳቫና እና የአል አሙዲ የግል እርሻዎች ላይ የመጀመሪያ ጉዳት ማድረሱን ጠቁመዋል፡፡ እንደ ክልል የተወሰኑ የመከላከል ቅድመ ዝግጅቶች መደረጋቸውን የገለጹት ሃላፊው፣ አርሶአደሩን የማንቃት ስራ መሰራቱንና በየወረዳው የመከላከል ግብረ ሃይል መቋቋሙን ተናግረዋል።
“የግሪሳ ወፍ መንጋ ወደ ትግራይ ክልል ገና ሲገባ፣ የቢሮው ባለሞያዎች ወደ ስፍራው ተልከው የዳሰሳና ሕዝቡን የማንቀሳቀስ ስራ ሲሰራ ቆይቷል።
የግሪሳ ወፍ መንጋ ብዛቱ መጀመሪያ ላይ አንድ ሚሊዮን እንደሚደረስ ተገምቶ ነበር። አሁን ላይ ግን የግሪሳ ወፍ መንጋው ብዛት ከአራት እስከ አምስት ሚሊዮን ይደርሳል” ብለዋል፣ ሃላፊው፡፡
የግሪሳ ወፍ መንጋው የመራቢያ አካባቢ አፋር ክልል፣ አዋሽ መሆኑን የሚናገሩት አቶ ሚኪኤለ፤ ነገር ግን የወፍ መንጋው ወደ ትግራይ የገባው ከአማራ ክልል ኮምቦልቻና ሸዋሮቢት አካባቢዎች ተነስቶ ነው ይላሉ፡፡ ግሪሳውን ለማባረር በአምቡላንስ የሳይረን ድምጾች ጭምር ታግዞ ከፍተኛ ድምጽ በማሰማት የመከላከል ስራ ሲሰራ መቆየቱን የሚገልጹት የሕዝብ ግንኙነት ሃላፊው፤ ከግብርና ሚኒስቴር በሁለት ቡድኖች የተዋቀሩ ባለሞያዎች ወደ ትግራይ ክልል መምጣታቸውንና ከክልሉ ባለሞያዎች ጋር በመናበብ አብረው እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ በተጨማሪም፣ ከግብርና ሚኒስቴር የተላኩ አራት መኪናዎች ከእነ ኬሚካል መርጫ መሳሪያዎቻቸው፣ ኬሚካሎችና ባለሞያዎቻቸው ጭምር ወደ ትግራይ ክልል መምጣታቸውንም አስታውቀዋል።
የኬሚካል ርጭት ለማካሄድ ከፍተኛ ዝግጅት ተደርጎ ለአይሮፕላን ማረፊያ የሚሆን ቦታ በመቐለ አካባቢ ለማዘጋጀት ወደ ስራ መገባቱን የገለፁት አቶ ሚኪኤለ፣ በህዳር 21፣ 23 እና 25 ሦስት ጊዜ የኬሚካል ርጭት መካሄዱን ተናግረዋል። “የተካሄደው ርጭት ውጤታማ ነው። ነገር ግን የግሪሳ ወፎቹ ብዛት ከፍተኛ ስለሆነ፣ በቶሎ ሊረግብ አልቻለም። አሁንም ሕብረተሰቡ በመከላከል ስራ ላይ ይገኛል።“ ብለዋል።
ሃላፊው አክለውም፤ የግሪሳ ወፍ መንጋው ከራያ ጨርጨር ተሻግረው ወደ አላማጣ አካባቢ እየገቡ መሆኑንና በግብርና ቢሮ በኩል ወደ አንድ ሺሕ ሄክታር መሬት አሰሳ ተደርጎ፣ 500 ሄክታር መሬት በግሪሳ ወፍ መንጋ ጉዳት እንደደረሰበት መረጋገጡን ጠቁመዋል። ሆኖም ግን በተለያዩ ጉዳዩ በሚመለከታቸው የተለያዩ ተቋማት ጥልቅ ምርመራ ከተደረገበት በኋላ፣ ስለደረሰው ጉዳት ሙሉ መረጃ እንደሚገኝና ይፋ እንደ ሚደረግ አቶ ሚኪኤላ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል።