
Administrator
“አለማችን ፕላኔታዊ ውሕደት ያስፈልጋታል”
--የመጀመሪያው ሁለንታዊ መድረክ በተዘጋጀበት አዳራሽ ውስጥ ከዓለም ሀገራት ተወክለው የመጡ ሰዎች እንዲሁም ባረኖች በረድፍ በረድፋቸው ተቀምጠዋል። የመድረኩ የአዘጋጅ ክፍል አባላት (እኔን ጨምሮ) የቅድመ አዳራሽ ሥነ ስርዓቶችን አስፈፅመናል፤ የትውውቅ፣ የቁርስ፣ የሙዚቃ፣ የፎቶና ቪዲዮ ትዕይንት… ሁሉም የቅድመ አዳራሽ መርሃ ግብር በስኬት ተከናውኗል። አሁን አዳራሹ ውስጥ ሁሉም የጥያቄና መልሱን መጀመር በብሩህ ስሜት፣ በኃይልና በንቃት ተሞልቶ እየጠበቀ ነው።
የመድረኩ ተቀማጮች ሰባት ናቸው፡ ሦስት ሰዎች፣ ሦስት ባረኖችና የሰዎች እና የባረኖች አማካይ የሆነቺው ሊሊት። ሊሊት የተቀመጠቺውም ሰዎች እና ባረኖች መካከል ነው። ሊሊትን ለማየት ያልጓጓ ማን ነው? በአፈታሪክ የተሳለልንን ያን ቁመናዋንና ቁንጅናዋን በምናባችን ይዘን ሁላችንም ሊሊትን እስክናይ ቋምጠን ነበር። እንደ ባረኖች ሁሉ እሷም ብርሃን ለብሳ ስናገኛት ግን የቆመው ልባችን ሳይረካ ቀረ። ….ሦስቱ ባረኖች ከግራ ወደ ቀኝ፡ የመጀመሪያዋ ባረን09 ትባላለች፣ ሁለተኛዋ ባረን217፣ ሦስተኛዋ ባረን199። ሦስቱም ባረኖች ፌደሬሽኑን ለመመሥረትና ለማስፋፋት ከፍተኛ ሥራ የሠሩና የሰው ልጅን በደንብ ያውቃሉ የሚባልላቸው ናቸው። ሲቆሙ ላስተዋላቸው ሴቶቹ ባረኖች ከወንዶቹ የሚረዝሙ ይመስላሉ፤ ድምፃቸው ከወንዶቹ ባረኖች ይልቅ ወፍራምና ሸካራ ነው። ብርሃናቸው ስለሚከልላቸው ፀጉራቸውን (ፀጉር ካላቸው) ያሳድጉ አያሳድጉ ባላውቅም፣ ሴቶችም ባረኖች እንደ ወንዶቻቸው ሁሉ ራሰ ከባድ ናቸው። ሰዎቹ የመድረኩ ተቀማጮች ደግሞ ከግራ ወደ ቀኝ በቅደም ተከተል በሁለንታዊ ስማቸው የመጀመሪያዋ ሂዩባረን77 ትባላለች፣ ሁለተኛዋ ሂዩባረን222፣ ሦስተኛው ሂዩባረን21። ሂዩባረን77 የጥቁር ጠይም የበሰለች ወጣት ሴት ናት፣ የሚያማምሩ ዐይኖችና ወከክ የሚያደርግ ፈገግታ ታድላለች፣ መናገር በጀመረች ቁጥር ቀድማ ፈገግታዋን እንደ መብረቅ ተግ ታደርጋለች። ሂዩባረን222 ፀጉሯ በግማሽ የሸበተ ሸንቃጣ ሴት ናት፣ ብሩህ ቡናማ ፊትና ውብ ሰማያዊ ዐይኖች አሏት። 77ቷና 222ቷ ሁለቱም ዋነኛ የትምህርትና የምርምር ዘርፋቸው በይነፕላኔታዊ ንፅፅራዊ ማህበረ-ፖለቲካዊ ምህንድስና ነው። ሂዩባረን21– የጥቁር ጠይሙ፣ ጎልማሳው፣ ሽበታሙ ሸበላ የመጀመሪያው ሁለንታዊ መድረክ ላይ የነበረው የኢንተርፕላኔታሪ ኮምንኬሽን ተቋምን የሚመራው ሰውዬ ነው።
የጥያቄና መልስ መርሃ ግብሩ ከመጀመሩ በፊት ሁሉም የአዳራሹ ሰው እና ባረን ለሊሊት ክብር ለአንድ ደቂቃ ተነስቶ አጨበጨበ። ሊሊት ተነስታ ሰግዳ አመሰገነች። ያቺ ሊሊት– የመጀመሪያዋ ሴት፣ እናም የመጀመሪያዋ እብሪተኛ– ሰውነቷን (እና ሴትነቷን) በራሷ ጥረት የፈተሸቺው– የፈለገቺውን ለማግኘትና የፈለገቺውን ለመሆን ቆርጣ ከገነት የወጣቺው ሊሊት። ሊሊት ቁመቷ ከባረኖቹ ይበልጣል፣ የሰውነቷ ቅርጽ እንደ ሰው ልጅ ሴቶች ቅርጽ ነው፣ ድምጿ ትንሽ ቢሻክርም እንደ ሰው ልጅ ሴት ድምፅ ቀጭንና አባባይ ነው። እውነት ሰው ናት? እውነት ሴት ናት? እውነት እንደ ሴት ልጅ የሚታቀፍ፣ የሚለስልስ፣ የሚሞቅ፣ የሚደማ ገላ አላት? ባየኋት።
በሊሊት የጉጉት ሀሳብ ስሸመጥጥ መድረኩ ተጀምሯል። ሁለተኛው ሁለንታዊ መድረክ ለሰው ልጅ እውነተኛ ስልጣኔና ህብረት እንቅፋት በሆኑ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ነበር። ጉዳዩ ለሰው ልጆች ሁሉ የሚጠቅም በመሆኑ መዝግቤ እነሆ አንብቡት እላችኋለሁ፡
ጠያቂ፡ በአፈታሪክ የምናውቃት ሊሊት እውነት ሆና ወደ ምድር በመመለሷ የተሰማኝን ስሜት የምገልፅበት ቃል የለኝም። የሁለቱ ፕላኔቶች እንዲሁም የሰው እና የባረን አማካይ እንደመሆኗ እኔ የመጀመሪያ የሆነውን ጥያቄዬን ማቅረብ የምፈልገው ለሊሊት ነው። ምድር ላይ ይሄን ፌደሬሽን የመሠረቱት ሰዎች እና ባረኖች አበክረው ሰዋዊና ፕላኔታዊ አንድነት ስለመመሥረት ይናገራሉ። የተወደድሽው እህታችን፣ ስለዚህ ጉዳይ ምን ትያለሽ?
ሊሊት፡ በመጀመሪያ አንድ አሳዛኝ እውነታ ልንገራችሁ፡ እስካሁን በሁለንታው ውስጥ ከማውቃቸው የአእምሮና የማሰብ ችሎታ ካላቸው ፍጡራን ውስጥ ዘራዊና ፕላኔታዊ አንድነት የሌለው የሰው ልጅ ብቻ ነው። ሌሎቹ የሰለጠኑ ፍጡራን ምንም ያህል ለሌሎች ለማይመስሏቸው ፍጡራን ክፉ ቢሆኑም እንኳን እርስ በርስ ግን አይጠፋፉም። የዚህ መሠረታዊ ምክንያቱ የሰው ልጅ ሰዋዊ አንድነት ከዚያም ፕላኔታዊ አንድነት አለመገንባቱ ነው። የሰው ልጅ ሰዋዊ አንድነት እንዳይኖረው ያደረገው ዋናው ምክንያት ደግሞ ራሱን በትናንሽ ማንነቶች ማጠሩ ነው። የሰው ልጅ አንድነት ጠላቶቹ ትናንሽ ማንነቶቹ ናቸው። እነዚህ ትናንሽ ማንነቶች ከሰው ልጅ መሠረታዊ ተፈጥሮ ያልመነጩ፣ የሰው ልጅ በሂደት በራሱ ላይ የጫናቸው ማንነቶች ናቸው። እነዚህ ትናንሽ ማንነቶች ለአብዛኛው የሰው ልጅ ችግር፣ መከፋፈልና ጦርነት መነሻዎች ናቸው። የሰው ልጅ የህዋ ስልጣኔን በጀመረበት በዚህ ዘመን እነዚህን ትናንሽ የማንነት ድርቶች አውልቆ መጣል አለበት። ስለ እነዚህ ትናንሽ ማንነቶች ዝርዝር በጉዳዮቹ ላይ ጥናት ያደረጉ ሰዎች እና ባረኖች እህት ወንድሞቼ የበለጠ የሚነግሩን ይሆናል።
ሊሊት ስትናገር ልክ እንደ ባረኖች ቃላቶቿ የአፏን እንቅስቃሴ ቀድመው ይወጣሉ፣ ተናግራ ስትጨርስ ወይ መሐል ላይ እልባት ስታደርግ ደግሞ ድምጿ ከአፏ እንቅስቃሴ ቀድሞ ያቆማል። እንግሊዝኛውን ታቀላጥፈዋለች። ከመቼው?
ጠያቂ፡ የሰው ልጅ ትናንሽ ማንነቶች የምትሏቸው የትኞቹን ማንነቶች ነው? ለስልጣኔና ለሰዋዊ አንድነት እንቅፋት ሊሆኑ የሚችሉትስ እንዴት ነው?
ሂዩባረን77፡ የሰው ልጅ ትናንሽ ማንነቶች ከፋፋይ ሃይማኖት፣ ጎሳ ነገድ ወይም ብሄረሰብ፣ የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም፣ የታሪክ ቅራሪ፣ የሀገር ድንበርና ብሔርተኝነት እንዲሁም የሰው ልጅን ውጫዊ አካላዊ ሁኔታን ወይም ቀለምን መሠረት ያደረጉ ማንነቶች ናቸው። እነዚህ ማንነቶች ከሰው እውነተኛ ተፈጥሮ ውጭ የሆኑ ሰው ሠራሽ ማንነቶች ናቸው። እነዚህ ማንነቶች የተቀባቡ የውሸት ሥሪቶች ናቸው፣ የሰው ልጅን በየቦታው እኛ እና እነሱ እያሉ ስለሚሸነሽኑ የሰዋዊ መስተጋብር ጋሬጣዎች ናቸው። እነዚህ ትናንሽ ማንነቶች የግብዝነት፣ የድንቁርና፣ የራስ ወዳድነት፣ የኢፍትሐዊነት፣ የመናቆርና የጦርነት መነሻዎች ናቸው። የሰው ልጅ በእነዚህ ትናንሽ ማንነቶች ውስጥ ሆኖ ዐይኑን ገልጦ እውነትን ለማየት አይችልም።
ሂዩባረን222፡ የሰው ልጅ ሲወለድ ንፁህ ነው፣ ሰው ብቻ ነው። እያደገ ሲሄድ በትናንሽ ማንነቶች ይቆሽሻል። መጀመሪያ በሃይማኖት ጣሳ ውስጥ ያስገቡታል፤ ከዚያ በጎሳ፣ በብሔረሰብና በሀገር ብሔርተኝነት ገመድ ይተበትቡታል፤ ከዚያ የታሪክ፣ የፖለቲካና የርዕዮተዓለም ሸክም ይጭኑታል። አደግሁ፣ በሰልሁ ሲል እውነቱን በእነዚህ ትናንሽ ማንነቶች ውስጥ አጥሮ ይገነባል። በዚህ አጥር ውስጥ እንደኳተነ በመጨረሻም እውነተኛ ማንነቱን ሳያውቅ ያልፋል። በከንቱ ማለፍ ብቻ አይደለም እነዚህ ትናንሽ ማንነቶቹን ለቤተሰቡና በዙሪያው ላሉት አውርሶ ነው የሚያልፈው። ሂደቱ አዙሪት ነው። እነዚህ ትናንሽ ማንነቶች እንደ ወሳኝ እውነታ ተቆጥረው በመሠረቱ አንድ አይነት ተፈጥሮና ፍላጎት ያለውን ሰው ከፋፍለው ሲያፋጁት ይኖራሉ።
ባረን199፡ እህቶቻችንና ወንድሞቻችን ስለሆኑት የሰው ልጆች የምናውቀውን ያህል በቅንነት እንናገራለን። የምንናገረው በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ ጣልቃ መግባት ስለምንፈልግ አይደለም፣ የምንናገረው ከሰው ልጅ ጋር ያለን ህብረት እንዲሰምር ነው። በህብረቱ እኛም የሰው ልጅም ተጠቃሚ ነን። ህብረታችን እንዲሰምር ታዲያ የሰው ልጅ ለእውነተኛ ስልጣኔው እንቅፋት የሆኑበትን ችግሮች መቅረፍ አለበት። እነዚህ ችግሮች እንዲቀረፉ ከሰዎች እህት ወንዶሞቻችን ጋር ተባብረን እንሠራለን፣ በገባን ልክ እንናገራለን። ከፋፋይ ሃይማኖት፣ ዘር ነገድ ወይም ጎሳ፣ ንዑስ ወይም ብሔረሰባዊ ብሔርተኝነትና የሀገር ብሔርተኝነት፣ ትናንሽና ትላልቅ የፖለቲካ ርዕዮተዓለሞች፣ ያለፈና የማይለወጥ ታሪክንና ትርክትን እየሳቡ እያመጡ በእሱ መነታረክና መከፋፈል… እነዚህና የመሳሰሉት ነገሮች በሰዎች መካከል የተሰነቀሩ ሰው ሰራሽ ድንበሮች ናቸው። የሰው ልጅ እውነተኛ ሞራላዊና ቁሳዊ ስልጣኔ ላይ የሚደርሰው እነዚህን የውሸት ድንበሮቹን አፍርሶ ሰዋዊና ፕላኔታዊ አንድነት ከፈጠረ ብቻ ነው።
ሂዩባረን21፡ ከሌላው የሰው ልጅ የሚለየንን ማንኛውንም ስብከት ልንቀበል አይገባም። በሰዎች መካከል የሚደረገውን ጋብቻ ከዝምድና በስተቀር የትናንሽ ማንነቶች አጥር ሊያግደው አይገባም። የጥላቻና የፖለቲካ ቀውስ አንዱ መነሻ ዘረኝነት ነው። የዘረኝነት መነሻችን አንዱ የመልካችን መለያየት ነው። የቀለማችንና የመልካችን ይሄን ያህል መለያየት አንዱ ምክንያት ደግሞ ቀደምቶቻችን ጋብቻቸውንና ዝምድናቸውን በጠባብ የማንነት ክበቦች ውስጥ አጥረው መኖራቸው ነው። የሰው ልጆች በነዚህ የውሸት ድንበሮች ሳንወስን እንገናኝ፣ እንተሳሰብ፣ እንጋባ እንዋለድ እንዛመድ። ያን ጊዜ ድንበሩና አጥሩ መፍረስ ይጀምራል፣ እውነተኛ ማንነታችን ይገለጣል፣ የሰላምና የፍትሕ መንገድ ይሰፋል። እርግጥ ነው ብዙ ሰዎች እነዚህን የውሸት አጥሮች እየዘለሉ ሲገናኙና ሲዛመዱ ኖረዋል። ሆኖም አጥሮቹ ተዘለሉ እንጂ ገና አልፈረሱም።
ጠያቂ፡ ሃይማኖት ሰው ከፈጣሪው ጋር የሚገናኝበት መንገድ ነው። ይሄን መንገድ እንዴት ይፍረስ ትላላችሁ?---
ከአዘጋጁ፡- በአብርሃም ገነት
ከተጻፈውና ሰሞኑን ለንባብ ከበቃው “ሳላዛት” የተሰኘ ረዥም ልብወለድ መጽሐፍ የተቀነጨበ ነው፡፡
የነብይ ገፅ
ከአድማስ ትውስታ ፤ 1993
ከትዝታ ፈለግ- 2 በግ ከአራጁ ጋር!!
ማእከላዊ እስር ቤት ያየሁትን ሁሉ ማስታወስ አልችልም፡፡ አንዳንድ የማልረሳቸውም አሉ፡፡-ጨለማ ቤት በገባሁ ማግስት ጥዋት ዶክተር ካሳሁን መከተን አወቅሁት፡፡
ማዕከላዊ - ታች ግቢ- 7 ቁጥር “ጨለማ ቤት” ይባላል፡፡ ነጥሎ (ለይቶ) ማስቀመጫ (Solitary confinement) ክፍል ነው፡፡ 7 ቁጥር ውስጥ አራት ትንንሽ ክፍሎች አሉት፡፡ መንግሥት “ቀንደኛ ፀረ- አብዮተኛ” የሚላቸውን የሚዘጋባቸው ክፍሎች ናቸው፡፡
እንደሰማሁት የእኔ ክፍል (Cell) ፍቅሬ ዘርጋው ከኢህአፓ ሰዎች አንዱ ነበረባት፡፡ ፍቅሬን ሕግ ትምህርት ቤት አውቀዋለሁ፡፡ እንደአጋጣሚ ካዛንችስ- ሼል ከፍተኛ 15 ቀበሌ 32 የተከራየሁት አፓርታማ የፍቅሬ ነበር፡፡ እኔ የመጣሁ እለት ለእኔ ክፍት ቦታ ለመፍጠር ይሆን ግጥምጥም ሆኖ፣ ፍቅሬ የዚያን ዕለት ማታ ተረሸነ፡፡ ሳስበው ይህ ነገር ከአጋጣሚ በላይ መሰለኝ፡፡ ሕግ ትምህርት ቤት… ካዛንችስ… ጨለማ ቤት አጉል መከታተል ነው፡፡ አካሄዱን አልወደድኩትም፡፡ ሊወድ የሚችልም ያለ አይመስለኝም፡፡ የእኔ ደወል የተደወለ መሆኑን ያሳያል፡፡
የ”ምናልባት ሕግ” (The law of probability) ከጨለማ ቤት በሁለት እግር ወጥቶ ለመሄድ ያለውን እድል አጨልሞ ያሳያል፡፡ ብርሃነ መስቀል ረዳ ጨለማ ቤት አድሮ ነው የተወሰደው፡፡ ቀኛዝማች ታዬ መሸሻም እዚሁ ነበሩ፡፡ ዓለም ሰገድና ጨርቆስ ደሞዝም እዚያው ጥቂት ሰንብተው ተሸኙ፡፡ እንዲህ ሲታይ ጉዳያችን “ጨለማ ቤት” ከደረስን በኋላ የሚወሰን አይመስለኝም፡፡ ተወስኖ አልቆ የምንገባ መሰለኝ፡፡ በዚህኛው ዓለምና በመቃብር መካከል ያለ ጊዜያዊ ማረፊያ (Half way house) መሆኑ ነው፡፡ የአንዳንዱ ሰው ጉዳይ ጨለማ ቤት ከደረሰ በኋላ የሚፈጥነው፣ የሚዘገየው በሌላ ሥራ ተጠምደው አላደርስ ብሎ ሳይሆን አይቀርም ብዬ አስባለሁ፡፡ የዚሁ ዓይነት ሥራ የሚሰራበት “ቄራ” ይኸኛው ብቻ ስለአልሆነ ሥራ ሊበዛ ይችላል፡፡
የቀኛዝማች ታዬ ከዚህ ለየት ይላል፡፡ ከ3 ዓመት በላይ ቆይተው ነው የተረሸኑት፡፡ ህግ ውስጥ “ይች ባትኖር” (But for) የሚሉት አላቸው፡፡ በምክንያቱና በውጤቱ መካከል ባለው ሁኔታ ላይ ተፅዕኖ የሚያሳድር ሐሳብ ነው፡፡ ወይ ያፈጥነዋል፣ ያዘገየዋል ወይም ግንኙነቱን ያቋርጠዋል፡፡
በቀኛዝማች መታሰር የተበሳጨ የወሎ ባላገር (ለቀው ሸሽተው ወሎ ገብተው ነበርና)፣ አንድ ወሎ የነበረን የደርግ አባል “ቀኛዝማችን አምጣ!” ብሎ ወጥሮ ሳይዘው አልቀረም፡፡ በዚህ መካከል በተፈጠረ ግርግር የደርግ አባል ወይ ሞቷል፣ ወይ ተጎድቷል፡፡ የሰማሁት ነውና እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ ይህ ለቀኛዝማች “But for” የሆነ ይመስላል፡፡ ይህ ባይኖር ኖሮ ላይገደሉም ይችሉ ነበር ማለት፣ ዋጋ የሌለው የአንጎል ጅምናስቲክ ነው፡፡ እውነቱ ተገደሉ ነው፡፡ እኒህን “… አምላክ ሰው… ሰውም አምላክ ሆነ…” የምላቸውን ቀኛዝማች ታዬን በሚመለከት አንድ ቀን መመለሴ አይቀርም፡፡
እኔ ከጨለማ ቤት በእግር ከወጡት ጥቂት እድለኞች ውስጥ ነኝ፡፡ የብርሃነ መስቀል ባለቤት ወ/ሮ ታደለች ወ/ሚካኤል እና መኪያ መሀመድ ሌሎቹ ናቸው፡፡ በኋላ እንዳጣራሁት ታደለች የተረፈችው ነፍሰ ጡር ስለነበረች ነው፡፡
እኔ ጨለማ ቤት አልጨለመብኝም፡፡ የመጨረሻ ቤቴ አድርጌ ስለተቀበልኩት፣ የመጨረሻ ጉዞውን ተቀብዬ፣ ለጉዞው ሥነ-ስርዓት ዝግጅት ላይ ነበርኩ፡፡ “አሟሟቴን አሳምርልኝ” ብዬ አልፀለይኩም፡፡ በእኔው እጅ ስለነበረ እኔው ላሳምረው ወስኜ ነበር፡፡ የመጨረሻው ጠሪ መጥቶ “አሰፋ ጫቦ ጋቢህን ይዘህ ውጣ!” ሲለኝ (ጋቢህን ይዘህ ውጣ ነው የሚባለው ለመጨረሻው ሲኬድ) በክብር፣ በውስጥ ህሊና ክብር ለመሄድ ነበር፡፡ ራሴን በራሴም፣ ሌላው በሚያየኝም፣ በማያየኝ ፊት ሳላዋርድ ለመጠናቀቅ ነበር፡፡ “የመጨረሻውን ጽዋ ለመጠጣት ከወሰኑ በዚያን በመካከሉ ያለው አያስጨንቅም፡፡ እኔን አላስጨነቀኝም፡፡” ትዕቢቴ ሽመልስን ይገርመው ነበር፡፡ በኋላ ወዳጄ የሆነው ጦር ሰራዊቱ መቶ አለቃ ሽመልስ ዋለልኝ የእስረኛ አስተዳዳሪ ነበር፡፡ በኢፊሴል ማነጋገር የምችለው እሱን ብቻ ነበር፡፡ ጨለማው ቤት ከዚያ በላይ እንዳይጨልም የብርሃን ጨረር ፈንጣቂ ነበር፡፡ ጨለማ ቤት አመት ከዘጠኝ ወር ተቀምጬ ላይ ቤት (ግቢ) ተዛወርኩ፡፡
ወሬ ሲሰማ “ጨለማ ቤት” ኋላ አዲስ አይነት የብርሃን ቤት ሆኖ ነበረ፡፡ የአዲስ አይነት ምርጥ እስረኞች (በጮሌነት ወይ በገንዘብ) መኝታ ክፍል ሆኖ ነበረ፡፡ እዚያ ከተማው ውስጥ ሴክሬቶ እንደምትሉት አይነት “ሰው ከቆየ ከሚስቱ ይወልዳል” ይላል ጎንደሬ፡፡ ሌላም ብሎ ሊሆን ይችላል፡፡ እኔ የሰማሁት ጎንደር ነው፡፡
ዶክተር ካሳሁን መከተ ጎንደሬ ነው፡፡ ዕድሜው ከ40 እና 50 መካከል የሚሆን ይመስለኛል፡፡ መካከለኛ ቁመት፣ ሽንቅጥ ሰውነት አለው፡፡ ቀይና መልከ መልካም ነው፡፡ ለወንድ ይባል እንደሁ አላውቅም እንጅ ቆንጆም ሊባል የሚችል ይመስለኛል፡፡ ሽቅርቅር ነው፡፡ አለባበሱ የተመጣጠነ፣ የተመዘነና ምርጥ ነው፡፡ የልብሶቹ አመራረጥ የሰከነና የጠራ (Seasoned) ነው፡፡ እንደዚያ አሳምሮና ተጠንቅቆ የሚለብስ ያየሁት ይኖራል፡፡ የማውቀው የለኝም፡፡ እስር ቤት፣ ያውም ጨለማ ቤት እንዲህ ከሆነ ውጭ እንዴትና እንዴት ያደርገው ይሆን? እያልኩ አስባለሁ፡፡
ዶክተር ካሳሁን የዋህ፣ ጅል፣ ግብዝ፣ ልታይ ልታይ ባይ፣ ግድርድር … ነው ለማለት እችላለሁ፡፡ እነዚህን ቃላት (ቅጽሎች) በመጥፎነት (Negatively) መጠቀሜ አይደለም፡፡ ይህ በብርቱ እንዲታወቅልኝ እፈልጋለሁ፡፡ ይልቁንም በበጎ ጎኑ (Positive) ነው፡፡ እነዚህ ባህርይ ገላጭ ቅጽሎች ሌላው ሰው ላይ ያለን የተለመደውን ትርጉማቸውን ይይዛሉ፡፡ ካሳሁን ላይ ግን ያንን ደረቅ ትርጉም (Generic connotation) የሚለቁ ይመስላሉ፡፡ ለቀውም አዲስ ለየት ያለ የራሱ ለዛ ያለው ትርጉም ይይዛሉ፡፡ ለእኔ የዋህነቱን ቅንነቱን መግለጫ ብሩህ ቀለማት ሆነዋል፡፡ ተሰባስበው አዲስ ውብ ዜማ ይፈጥራሉ፡፡ አዲስ ማህሌቶች አዲስ ሽብሸቦ ይሆናሉ፡፡ ለየት ያለ ባህርይ መግለጫ ይሆናሉ፡፡ እኔ እንደ አየሁትና መግለጽ እንደሞከርኩት ማለት ነው፡፡
ዶ/ር ካሣሁን ጎንደሬ ነው ብያለሁ፡፡ ግድርድርም ነው ብያለሁ፡፡ ይህ ስለጎንደሬ ከምናውቀው ወይም እናውቃለን ከምንለው ጋር የሚሄድ አይመስለኝም፡፡ ከመሳዩ፣ ከተምሳሌቱ (Stereotype) ጋር አይሄድም፡፡ የራሱ የካሳሁን ለዛ አለው፡፡ አዲስ ለከት ይሰጠዋል፡፡ በዚህ በአውሮፓ ታሪክና ሥነ-ጽሁፍ ውስጥ (Chivalry) የሚሉት መልክ አለው፡፡ ወይም የሴርቫንተሰን (Miguel de Cervantes) ዶን ኪሆቴን (Don Quixote) የሚመስል ባህርይ አለው፡፡ ገራገርና ዘራፌነት ያለው ነው፡፡
ዶ/ር ካሣሁን የታሰረው በስለላ ተጠርጥሮ ነው፡፡ ለሲ.አይ.ኤ በመላው ዓለም፣ በኢትዮጵያም ሰላዮች እንዳሉት የታወቀ ነው፡፡ ኢትዮጵያን ለማጥፋት፣ ለመበታተንና ዛሬ የደረሰችበት ለማድረስ በብዙ ወኪሎቹ (Proxies) በኩል ብዙ ሚሊዮን ዶላር እንዳወጣ ዛሬ የአደባባይ ሚስጥር ነው፡፡ እርግጥ አደባባይ አንወጣም፤ ሚስጥሩም አይውጣብን የሚሉ አሉ፡፡ የወኔ ጉዳይ ነው፡፡ ዶ/ር ካሣሁን ሰላይ ሆኖ ሊሆን ይችላል፡፡
ዶ/ር ካሣሁን ሰላይ ቢሆን እንኳ መሆኑን የሚያውቅና የሚረዳ አይመስለኝም፡፡ ነገርን መታየት ከሚገባ ዘርፍና አንፃር ማየት አይችልም፡፡ ያመነውን ያሰበውን በዘፈቀደ እንደልቡ ይናገራል፡፡ ይህንንም እንደ-ጀግንነት ይቆጥረዋል፡፡ እንዲደነቅለትም ይፈልጋል እንጂ የነገርን አመጣጥ መነሻ፣ መድረሻ ሊያስከትለው የሚችለውን ችግር ማጣጣም የሚችል አይመስልም፡፡
ሌላም የሚደንቀኝ የዶ/ር ካሣሁን ነገር ነበር፡፡ የገባበትን ማጥ በቅጡ የተረዳው አይመስልም፡፡ “ጨለማ ቤት” መቀመጡን “ለክብሩ የተደረገ” አድርጎ ገምቶትም ሊሆን ይችላል፡፡ እንዴትና በምን መንገድና ትንታኔ ከዚያ እንደደረሰ ማወቅ ይቸግራል፡፡ ይህ ነው ከብዙዎቻችን ለየት ይላል የሚያሰኘኝ፡፡ ይህ ነው (Don Quixote) የሚመስል ባህርይ አያጣም የሚያሰኝ፡፡
ስለተከሰሰበት ጉዳይ በቀጥታ ልጠይቀው ሞክሬአለሁ፡፡ በተዘዋዋሪም ሞክሬአለሁ፡፡ ውጤቱ ያው ነው፡፡ ንቆ አናንቆ አቃሎ ይነግረኛል፡፡ ከመጤፍ አልቆጠራትም፡፡ ይልቁንም ከጥዋት እስከ ማታ ስለ አለባበሱ ስለ መሽቀርቀሩ ሲጨነቅ ይውላል፡፡ አንዳንዴ ልብስ በቀን ሦስት ጊዜ ይቀይራል፡፡ ማዕከላዊ ጥያቄው ማን ምን ለበሰ? አይደለም፡፡ ዛሬ ደግሞ የማን ተራ ይሆን? የሚል ነው፡፡ ጋቢህን ይዘህ ውጣ - የሚባል ማን ይሆን? የሚል ነው፡፡ ለበሰ፣ ራቁቱን ሄደ ተመልካች የለውም፡፡
ዶ/ር ካሣሁን አንዳንዴ ለምርመራ ጥዋት ሄዶ ለምሳ ይመለሳል፡፡ እንደሌላው በታረሰ እግር እየዳኸ ሄዶ ደም እያዘራ አይመለስም፡፡ እየሳቀ ሄዶ እየሳቀ ይመለሳል፡፡
እንዴት እንደዋለ፣ ምርመራው ከምን እንደደረሰ ስጠይቀው መልሱ ያው ነው፡፡ በጣም ስለጨቀጨቅሁት እንደመቀያየም፣ መኮራረፍም ጀምረን ነበር፡፡ ወይም “ጓድ መቆያ መርማሪው ጋር ቡና ጋብዞኝ ስንጫወት ዋልኩ” ይለኛል፡፡ “ዶሮን ሲያታልሏት” መሆኑን ተረድቻለሁ፡፡ ላስረዳው ግን አልቻልኩም፡፡
ዶ/ር ካሣሁን ትምህርቱ የቤተ ክህነት (Theology) ይመስለኛል፡፡ ለዚሁ ትምህርት ቱርክ ወይም ግሪክ ወይም ሁለቱም ጋር ሄዶ የመጣ ይመስለኛል፡፡ ብዙዎች እንደዚህ እየሄዱ ሌላ ማህበራዊ ሳይንስ (Social Science) ተምረው እንደሚመለሱ አውቃለሁ፡፡ ካሳሁን እንደዚያ ማድረግ አለማድረጉን አላውቅም፡፡ ከውጭ የሚታይ የለም፡፡
በቀን ቢያንስ አንዴ ሳያነሳ የማይውላቸው ሁለት ነገሮች አሉ፡፡ አንደኛው ስለደባርቅ-ዳባት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኋላቀርነት ማስረጃ ያደርጋቸዋል፡፡ እስከ ዛሬ መብራት እንኳ አልገባላቸውም፡፡ ሶሻሊዝም ሶሻሊዝም ይላሉ፤ ደባርቅ መቼ መብራት ገባ ይላል፡፡ ይህችው ነች፤ አትለወጥም፡፡
ሌለው የሚያወራው አዲስ አበባ አራት ኪሎ ስለሚያውቃቸው ጉራጌ ሴት ነበር፡፡ ምግብ ቤት ያላቸው፡፡ አሁን ያሉት አቃቂ መዳረሻ ዳገቱ ላይ ነው፡፡ እናቴ ይላቸዋል፣ የሀገር እናት ይላቸዋል፡፡ ከዚህ ውጪ ስለዘመድ አያነሳም፡፡ ብዙ ያለውም አይመስለኝም፡፡ ዶ/ር ካሳሁን ያገባ የወለደም አይመስለኝም፡፡ ዋቢ ሸበሌ ሆቴል እኖራለሁ ያለኝ መሰለኝ፡፡
የወደቀበት ክብደቱን ቢያውቀው የሚለውጠው ላይኖር ይችላል፡፡ ሆኖም ቢቻል ማወቅን የመሰለ ያለ አይመስለኝም፡፡ አይኑን አፍጥጦ የመጣበትን ሳይረዳ ሰንብቶ አንድ ቀን ዶ/ር ካሣሁን ጋቢህን ይዘህ ውጣ ተባለ፡፡ በመጨረሻ የሚሄዱትን “ጋቢህን ይዘህ” ይባላል፡፡ መገነዣ ይሆን? እነብርሃነ መስቀል የተጠሩ ቀን መሰለኝ ዛሬ “ቡና ተጋብዞ” አልተመለሰም፡፡ ወደ ጨለማ ቤትም አልተመለሰም፡፡ ወዴትም አልተመለሰም፡፡ ንጹህ በግ ከአራጆቹ ጋር ሰንብቶ ተሰዋ፡፡ በራዲዮም ተነገረ፣ የብዙ ሰው መገደል ያሳዝነኛል፡፡ የዶ/ር ካሳሁን የባሰ ከሚያሳዝነኝ ውስጥ ነው፡፡
****
(አዲስ አድማስ፤ ታህሳስ 7 ቀን 1993 ዓ.ም)
የወቅቱ ጥቅስ
“ትላንት ቢያመልጠኝ ዛሬ አለልኝ የማይልና አዎንታዊ እልህ የሌለው መሪ ከስህተቱ አይማርም፡፡ ከስህተቱ ባልተማረ ቁጥር አገሩን ከድጡ ወደ ማጡ እየከተተ ህዝቡን ለባሰ ችግር ይዳርጋል፡፡”
“ለብቻዬ ስንጥር ከምሆን ከሀገር ጋር እርፍ ልሁን”
አንድ ልዑል ከቤተ-መንግስት ራቅ ብሎ ወደሚገኝ አንድ ትልቅ ጫካ ሄዶ አደን ሲያድን ውሎ ወደ ቤተ-መንግሥቱ ሲመለስ አንድ ባላገር ያገኛል፡፡ ባላገሩ ልዑሉ ማን እንደሆነ አያውቅም ነበርና አንዳችም እጅ- ሳይነሳ፣ ሰላምታም ሳይሰጥ ዝም ብሎ መንገዱን ይቀጥላል፡፡ ልዑሉም የባላገሩ ነገር ገርሞት፣
“ሰማህ ወይ ወዳጄ፣ ለመሆኑ እኔ ማን እንደሆንኩ ታውቃለህ ወይ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ባላገሩም፤ “በመንደራችን ባለው ጫካ ውስጥ በገዛ-ፈቃድህ ገብተህ አደን ስታድን እንደቆየህ አይቻለሁ፡፡ በሰላም የተቀመጡትን አዕዋፋት ስትረብሻቸው፣ እንስሳቱንም መጠጊያ ስታሳጣቸው የነበርክ ሰው መሆንህንም ተመልክቻለሁ” አለው፡፡
ልዑሉም፤ “ምን ስሰራ እንደቆየሁ ማወቅህ መልካም፡፡ ማንነቴንስ አውቀሃል ወይ?”
ባላገር፤ “አላውቅም፡፡”
ልዑሉ፤ “እንግዲያው ና ፈረሴ ላይ ውጣና አብረን ወደ ከተማ እንሂድ፡፡ ንጉሥ ማለት ምን እንደሆነ እዚያ ታውቃለህ” አለው፡፡
ልዑሉ ባላገሩን አፈናጦት ወደ ከተማ ይዞት ሄደ፡፡ በመንገድ ላይም “ንጉሥ ማለት የተከበረ፣ በሄደበት ቦታ ሁሉ ህዝብ እጅ የሚነሳው፣ መንገደኛው ሁሉ ቆሞ የሚያሳልፈው ትልቅ ሰው” ነው አለው፡፡
ከተማ ሲደርሱ፤ ህዝቡ ልዑሉን ሲያይ እየቆመ፣ እጅ እየነሳ አሳለፈው፡፡ ግማሹም አቤቱታውን አሰማ፡፡
ይሄኔ ልዑሉ ወደ ባላገሩ ዞሮ፤ “አሁንስ ንጉሡ ማን እንደሆነ አወቅህ?” ንጉሡ ማን ይመስልሃል?” ሲል ጠየቀው፡፡
ባላገሩም፤ “እንግዲህ፤ ወይ እኔ ወይ አንተ መሆናችን ነዋ” ሲል መለሰ፡፡
“ቡመራንግ” ማለት ይሄው ነው - ለሌላው የወረወሩት ቀስት ተመልሶ ወደ ራስ!
* * *
ህዝቦችና መሪዎች ሲጠፋፉ የሚፈጠረው ግራ-መጋባት አይጣል ነው! የክልል፣ የቀጠና፣ የወረዳና የቀበሌ መስተዳድር. የቢሮና የሚኒስቴር ኃላፊዎች እንዲሁም የፖለቲካ ፓርቲዎችና መሪዎች ከህዝብ ሲርቁ ከላይ እንደተጠቀሰው ባላገር ማንነታቸው ብቻ ሳይሆን ምንነታቸውም ለህዝብ ግራ የሚገባበት ደረጃ ይደርሳል፡፡ ህዝቡ ልቡ ክፍት ነው፡፡ ህዝብ የነገሩትን ይሰማል፡፡ የተረጎሙለትን፣ እውነት ብሎ ይቀበላል፡፡ ያወጁለትን አዋጅ፣ ይበጀኝ ብሎ ያከብራል፡፡ የደነገጉለትን ህግ፣ በወጉ ሊተዳደርበት ይነሳል፡፡ ያወጡለትን መመሪያ እመራበታለሁ ብሎ ይስማማል፡፡ እቅዶች አምረው ሲያያቸው ሰምረው አገኛቸዋለሁ ብሎ ተስፋ ያደርጋል፡፡ ችግር የሚፈጠረውና ፀብ የሚመጣው፣ አንድም በተግባር ሲተረጎሙ በመዛባታቸው፤ አንድም ባወጣቸው ክፍል በራሱ በቃል-አባይነት እንደሌሉ ሲካዱ (ሲሻሩ) ነው፡፡ “Law-maker Law-breaker” እንዲል ፈረንጅ፡፡ ያስቡልኛል ያላቸው መሪዎችና ኃላፊዎች “አንተና አንቺ” ብለው ከናቁት፣ ያወጡትን መመሪያዎች በሱው ላይ መጠቀሚያ ካደረጓቸው፣ በግልፅ-ወገናዊነት “ሁሉም ህዝቦች እኩል ናቸው ካሉት፣ አንዳንዶቹ ግን የበለጠ እኩል ናቸው” ካሉት፣ አዋጅም፣ ህግም፣ መመሪያም እንደ ብዙዎቹ ተግባር-አልባ የፕሮጄክት ጥናቶች ያማሩ ወረቀቶች ሆነው ነው የሚቀሩት፡፡
እቅድ በሥራ ላይ መዋሉን ለማየት በሚል “የግምገማ” ስብሰባ፣ ጥንት የሚታወቀው “ድርጅታዊ አሰራር” ከተንፀባረቀ፣ “በእኔ አስተያየት” በሚል የግል ካባ ቡድናዊ ስሜት የሚያስተጋባ ከሆነ አመራርና ተመሪ መራራቁ የማይቀር አባዜ ይሆናል፡፡ ህዝብን በግምገማ ማረቅ አይቻልም! መሪዎችንና መመሪያዎችን እንጂ! እነሱም በጄ ካሉ! ግምገማውም የዕውነት ከሆነ! በአንድ ወቅት ስለ ሂስና ግለ-ሂስ ሲወሳ፤ ”ሂስ እያሉ ሌላውን መዘርጠጥ፣ ግለ ሂስ እያሉ ራስን ማዋረድ አይገባም!” ያሉ እንደነበሩ ያስታውሷል፡፡ መታረም መተራረም፣ መቻል፣ መቻቻል የሚቻለው ትክክለኛ ሂስ ማቅረብ ሲቻል ነው፡፡ እዚህ ጋ ድክመት አለ ተብሎ ሲጠቆም ነው፡፡
እርግጥ ነው መማማር ያስፈልጋል፡፡ ሆኖም ትምህርቱ መታወቅ፣ አስተማሪና ተማሪውም አስቀድሞ መለየት አለበት፡፡ ገጣሚው ኦማር ካህያም እንዳለው፤ “እኔስ ማነኝሳ ቁጭ ብዬ እምማር፤ አንተ ማነህ እሱን የምታስተምር፤” ሳንባባል ለመቀጠልና ለመማማርም መቻቻል አለብን፡፡ አለበለዚያ አንድ አዋቂ የሀገራችን ፀሐፌ-ተውኔት ባንደኛው ቴያትራቸው ውስጥ እንደፃፉት ይሆናል፡፡
አንዱ ገፀ-ባህሪ፤ “ምነው ተጠፋፋን ጓድ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡
ጓዱም ሲመልስ፤ “የአብዮት ጊዜ አይደለም እንዴ? መጠፋፋት መች ገደደ?!” ነበር ያለው፡፡
ይህን መሰል የፖለቲካ ሰዎች ፈሊጥ ህዝብ ውስጥ እንዲገባ መደረግ የለበትም፡፡ ህዝቦች እንዲኖሩ እንጂ እንዲጠፋፉ፣ እንዲቻቻሉ እንጂ እንዲናቆሩ መሆን የለባቸውም፡፡ ቅን ልቦና፣ ፅናትና ለሀገር ማሰብ ሲኖር መቻቻል ይቻላል፡፡ መሪዎችና የፖለቲካ ድርጅቶችም ቢሆኑ መቻቻል ይችላሉ፡፡
ዋናው፤ “ለብቻዬ ስንጥር ከምሆን ከሀገር ጋር እርፍ ልሁን!” ማለት ብቻ ነው፡፡
የአሜሪካ ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት የገንዘብ ድጋፍ መቋረጥ የሃብት ክፍተት መፍጠሩ ተገለጸ
በቅርቡ የአሜሪካ ዓለምአቀፍ ተራድዖ ድርጅት (ዩኤ.ስኤ.አይ.ዲ) የገንዘብ ድጋፍ ማቋረጡን ተከትሎ፣ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች ላይ የሃብት ክፍተት መፍጠሩ ተነገረ፡፡ ችግሩን ለመፍታት መንግሥት አስፈላጊ እርምጃዎችን እንዲወስድ ተጠይቋል።
ይህ የተነገረው የኢትዮጵያ ሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት ባለፈው ረቡዕ የካቲት 5 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ ላይ ሲሆን፣ ከገንዘብ ድጋፉ መቋረጥ በኋላ የተፈጠሩ ክፍተቶችን ለመቅረፍ እያከናወናቸው ስለሚገኙ ስራዎች በዚሁ መግለጫ ላይ አትቷል። ምክር ቤቱ ሁኔታዎችን በአትኩሮት እየተከታተለ እና ለጉዳዩ እልባት “ይሆናሉ” የተባሉ እርምጃዎችን እየወሰደ እንደሚገኝ አስታውቋል።
በዓለም አቀፍ ደረጃ የአሜሪካ ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት (ዩ.ኤስ.ኤ.አይ.ዲ) ፕሮጀክቶች መቋረጣቸው በኢትዮጵያ በሚንቀሳቀሱ በርካታ የሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ስራ ላይ ከፍተኛ አሉታዊ ተጽዕኖ ማሳደሩን ምክር ቤቱ ገልጿል። አክሎም፤ “የምክር ቤቱ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴና የጽሕፈት ቤቱ አመራሮች ከሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን አመራሮች ጋር ተገናኝተው፣ የፕሮጀክቶች ድንገተኛ መቋረጥ የሚያስከትሉትን ክፍተቶች ለመቅረፍ መክረዋል” ሲል አብራርቷል።
ምክር ቤቱ በመንግሥት በኩል አስፈላጊ የመፍትሄ እርምጃዎች እንዲወሰዱ መጠየቁን አመልክቶ፣ “የዩ.ኤስ.ኤ.አይ.ዲ የገንዘብ ድጋፍ በድንገት መቋረጡ በዚህ ድጋፍ ላይ ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል ይደገፉ የነበሩ የሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶችና የሚያገለግሏቸው የማሕበረሰብ ክፍሎች በተለየ ሁኔታ በሚያደርጉት የልማት፣ የሰብዓዊ ድጋፍና የዲሞክራሲ ሥራ ላይ የሃብት ክፍተት ፈጥሯል” ብሏል፡፡
ምክር ቤቱ በዘርፉ ላይ የሚደርሰውን አሉታዊ ተፅእኖ መጠን በትክክል ለመረዳት አጠቃላይ የተፅዕኖ ግምገማ እንዲካሄድ መጠየቁን በመጥቀስ፣ ግምገማው መካሄድ መጀመሩንና በግምገማውም ተጽዕኖ ላይ የወደቁ ተቋማት ብዛት፣ የፕሮጀክቶች አይነት፣ ከአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት ተመደቦ የነበረ በጀት፣ የተጠቃሚዎች (የተረጂዎች) ቁጥርና እየተከናወኑ ያሉ ተግባራት ላይ ሊመጡ የሚችሉ ጉዳቶችን ጨምሮ ሌሎች “አስፈላጊ ናቸው” ተብለው የተለዩ መረጃዎች በሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን እየተሰበሰቡ እንደሚገኙ በመግለጫው ላይ ጠቅሷል።
“ግምገማው ከተጠናቀቀ በኋላ የሲቪል ማሕበረሰብ ዘርፉ ተወካዮች፣ የመንግሥት አካላት፣ የልማት አጋሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ይፋ ተደርጎ ምክክር በማድረግ ቀጣይና ዘላቂ የመፍትሄ ሃሳቦች ተሰብስበው አፋጣኝ እርምጃ እንደሚወሰድ ይጠበቃል” ያለው ምክር ቤቱ፣ የሲቪክ ማሕበረሰብ ድርጅቶች በግምገማው ላይ ንቁ ተሳታፊ እንዲሆኑ ጥሪ አቅርቧል።
የኢትዮጵያ ሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት በአሜሪካ ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት (ዩ.ኤስ.ኤ.አይ.ዲ) የገንዘብ ድጋፍ መቋረጥ ምክንያት ለተጎዱ ድርጅቶች አማራጭ የገንዘብ ምንጮችን የሚያፈላልግ ቡድን እንዳቋቋመ መግለጹ የሚታወስ ነው። በዚሁ ቡድን አማካይነትም የተጎዱ ድርጅቶች አማራጭ የገንዘብ ምንጮችን የሚያገኙበትና ችግሩን የሚቋቋሙበትን መንገድ እንደሚያፈላልግ ምክር ቤቱ አስታውቋል፡፡
በአማራ ክልል የትምህርት ዘርፉ ዕድገት ከዜሮ በታች እንደሆነ ተገለጸ
59.8 በመቶ የሚሆኑ ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ውጪ ሆነዋል
በአማራ ክልል በ2016 በጀት ዓመት የትምህርት ዘርፉ ዕድገት ከዜሮ በታች እንደሆነ የገለጹት የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ፤የትምህርት ዘርፉ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት ተናግረዋል፡፡
የአማራ ክልል ምክር ቤት 6ኛ ዙር፣ 4ኛ ዓመት የስራ ዘመን፣ 9ኛ መደበኛ ጉባዔ ከየካቲት 4 እስከ 7 ቀን 2017 ዓ.ም. የተካሄደ ሲሆን፤ በጉባዔው የመጀመሪያ ቀን የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ለምክር ቤቱ አባላት የስድስት ወራት የስራ አፈጻጸም ሪፖርት አቅርበዋል። በዚሁ ሪፖርት ላይ ትኩረት ያደረጉበት ጉዳይ የትምህርት ዘርፍ ነበር።
ርዕሰ መስተዳድሩ በአማራ ክልል የትምህርት ዘርፉ ከፍተኛ ጉዳት እንደደረሰበት አመልክተዋል። በተለይም ከ2015 ዓ.ም. ጀምሮ የዘርፉ የዕድገት ምጣኔ ከዜሮ በታች እንደሆነ አስረድተዋል።
የዕድገቱ ማሽቆልቆል ዋነኛው ምክንያት በክልሉ ከሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት አንስቶ በተከታታይ የተፈጠሩ የጸጥታ ችግሮች መሆናቸውን የተናገሩት አቶ አረጋ ከበደ፤ “በዚሁ ችግር ምክንያት ተማሪዎች ወደ ትምህርት ቤት መምጣት አልቻሉም” ብለዋል። አክለውም፤ “ይህ ሁኔታ የትውልድ ቅብብሎሽን የሚገታ ታላቅ ስብራት ነው” ሲሉ አጽንዖት ሰጥተዋል።
“የትምህርት ዘርፉ ከፍተኛ ትኩረት የሚያስፈልገው ነው” ያሉት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ ባለፉት ስድስት ወራት ውስጥ የትምህርት ዘርፉ የደረሰበትን ደረጃ አብራርተዋል፡፡ በዚህም 4 ሺህ 965 የመማሪያ ክፍሎችን ለመገንባት ታቅዶ፣ 2 ሺህ 210 ክፍሎች እንደተገነቡ ጠቁመው፤ ከዕቅዱ 44 ነጥብ 5 በመቶ ማሳካት መቻሉን ተናግረዋል።
ከዚህም በተጨማሪ፣ 8 ሺህ 882 ክፍሎች ጥገና እንደተደረገላቸው፣ ከእነዚህም ውስጥ 5 ሺህ 136 የመማሪያ፣ 3 ሺህ 746 የአስተዳደር አገልግሎት የሚሰጡ መሆናቸውን ርዕሰ መስተዳድሩ አብራርተዋል። 38 ሺህ 442 ለመማር ማስተማር ስራ የሚያገለግሉ ጠረጴዛዎችን ለማቅረብ ታቅዶ፣ 19 ሺህ 445 ጠረጴዛዎች ማቅረብ ስለመቻሉ፣ ይህም ከተያዘው ዕቅድ አንጻር 51 በመቶ ለማሳካት መቻሉን ገልጸዋል።
ከመጽሐፍት ሕትመት ጋር በተያያዘ በክልሉ በጀት 4 ሚሊዮን 22 ሺህ 473 መጽሐፍት መታተማቸውንና 3 ሚሊዮን 17 ሺህ 249 ያህሉ መሰራጨታቸውን ጠቁመዋል። በዚህም ከተያዘው ዕቅድ ጋር ሲመዘን፣ 75 በመቶ ያህል መሳካቱን ነው ያስረዱት።
በሌላ በኩል፣ በትምህርት ሚኒስቴር አማካይነት 6 ነጥብ 6 ሚሊዮን መጽሐፍት ታትመው፣ 4 ነጥብ 1 ሚሊዮን ያህሉ መሰራጨታቸውን የጠቆሙት ርዕሰ መስተዳድሩ፤ ይህም ከተያዘው ዕቅድ አንጻር ሲመዘን 61 በመቶ ተሳክቷል ብለዋል። ይሁን እንጂ በወቅታዊው የጸጥታ ችግር ሳቢያ የመጽሐፍት ስርጭቱ ፈተና እንደገጠመው አስታውቀዋል።
“በስርጭት ወቅት የገጠሙ ችግሮችን በመቋቋም የመማሪያ መጽሐፍትን ጨምሮ የተለያዩ የትምህርት መርጃ መሳሪያዎችን ማስራጨት ተችሏል” ያሉት አቶ አረጋ ከበደ፤ የታተሙ መጽሐፍት ለስርጭት በሚጓጓዙበት ወቅት የእሳት ቃጠሎ የደረሰባቸው እንዳሉ አመልክተዋል፡፡ ነገር ግን ይህንን ተግባር የፈጸመው የትኛው ወገን እንደሆነ አልገለጹም፡፡
በአማራ ክልል 10 ሺህ 983 የቅድመ አንደኛ፣ መካከለኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንደሚገኙ አውስተው፣ ከእነዚህ ውስጥ መደበኛ የመማር ማስተማር ስራቸውን እያከናወኑ ያሉት 7 ሺህ 44 ትምህርት ቤቶች ወይም 67 ነጥብ 7 በመቶው ብቻ መሆናቸውን ገልጸዋል። መደበኛ ስራቸውን ያቋረጡ ትምህርት ቤቶች ብዛት 3 ሺህ 466 እንደሆኑም ጠቅሰዋል።
“ከ7 ሚሊዮን በላይ ተማሪዎች በትምህርት ገበታ ላይ እንዲገኙ ቢታቀድም፣ 2 ሚሊዮን 786 ሺህ 483 (ወይም 40 ነጥብ 2 በመቶ) ብቻ ናቸው እየተማሩ የሚገኙት ያሉት አቶ አረጋ፤ 59 ነጥብ 8 በመቶ የሚሆኑት ተማሪዎች ከትምህርት ገበታ ውጪ እንደሆኑ ገልጸዋል።
ይህም ከወቅታዊው የጸጥታ ችግር የተያያዘ መሆኑን ርዕሰ መስተዳድሩ ቢናገሩም፣ ለምክር ቤቱ አባላት ባቀረቡት ማብራሪያ ግን በአማራ ክልል “እየተሰራ ነው” ያሉት የሰላም ማስፈን ስራ ስኬታማ መሆኑንና ከተወሰኑ አካባቢዎች በስተቀር በአብዛኛው የአማራ ክልል ሰላም ማስፈን መቻሉን ነው የጠቆሙት፡፡
የኢህአፓ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባሉ ታሰሩ
የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አቶ ይሳቅ ወልዳይ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ለእስር እንደተዳረጉ ተጠቆመ። ፓርቲው ከመንግሥት የሚደርስበት ጫና ከጊዜ ወደ ጊዜ እየበረታ መምጣቱንም ገልጿል።
ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባሉ አቶ ይሳቅ የታሰሩት ሐሙስ የካቲት 6 ቀን 2017 ዓ.ም. በፓትሮል መኪና በመጡ የፌደራል ፖሊስ አባላት ሲሆን፣ መኖሪያ ቤታቸው እንደተፈተሸም የኢህአፓ ተቀዳሚ ሊቀ መንበር መጋቢ ብሉይ አብርሃም ሃይማኖት ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል። ጠዋት ላይ መኖሪያ ቤታቸው ከተፈተሸ በኋላ፣ የፌደራል ፖሊስ አባላት ከቀኑ 6:30 ወዳልታወቀ ቦታ “ወስደዋቸዋል” ብለዋል።
እስካሁን አቶ ይስሃቅ የተወሰዱበትን ቦታ ማረጋገጥ እንዳልተቻለ የገለፁት ሊቀመንበሩ፤ ፓርቲው የታሰሩትን ቦታ እያጣራ እንደሚገኝ ተናግረዋል።
የአቶ ይሳቅ የእስር መነሻ የፖለቲካ አመለካከታቸው መሆኑንና ከዚህ በፊት ለእስር ተዳርገው እንደነበር በማውሳትም፣ ይሁንና ከተወሰኑ ሰዓታት እስር በኋላ እንደተፈቱ ተናግረዋል። ከእስር ባሻገር፣ ከመንግስት የጸጥታ አካላት የተለያዩ የግድያ ዛቻዎችና ማስፈራሪያዎች እንደሚደርሳቸውና ይህንንም ሁኔታ ለፓርቲው ጽሕፈት ቤት ማሳወቃቸውን ገልጸዋል።
“መንግስት ኢሕአፓ ላይ በጣም ትኩረት እያደረገ ነው። በኦሮሚያ ክልል ብዙ አባሎቻችን ታስረዋል። በሐረር ክልል አንድ የፓርቲያችን አመራር ታስሮ ተፈትቷል።” ያሉት መጋቢ ብሉይ፣ “ኢሕአፓን ከፖለቲካ ዕንቅስቃሴው ለማስቆምና የሕዝብ ድምጽ እንዳይሆን ለማድረግ ነው እነዚህን ድርጊቶች የሚፈጸሙት።” በማለት አስረድተዋል።
“አሁንም በሰላማዊ ትግል ላይ ጽኑ ዕምነት አለን” የሚሉት መጋቢ ብሉይ አብርሃም፣ “ሕገ መንግስቱ የሚፈቅድልን ከመቶ በላይ የሰላማዊ ትግል ዓይነቶች አሉ” በማለት ተናግረዋል። ይሁን እንጂ ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ ፓርቲያቸው ቢሞክርም፣ በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች የእመቃ ዕርምጃ እንደተወሰደና እርሳቸውን ጨምሮ ሌሎች የፓርቲው አመራሮች ለወራት ታስረው መቆየታቸውን አብራርተዋል።
ተቀዳሚ ሊቀ መንበሩ፤ “ኢሕአፓን ባሳደዱት ቁጥር እየጠነከረ የሚመጣ ድርጅት ነው። ትግላችንን አጠናክረን እንቀጥላለን” ሲሉ ለአዲስ አድማስ ተናግርዋል።
ሩሲያና ዩክሬን በአፋጣኝ ድርድር ለመጀመር መስማማታቸውን ትራምፕ አስታወቁ
• ፕሬዚዳንት ትራምፕና ፑቲን በሳኡዲ ተገናኝተው ሊወያዩ ነው
የአሜሪካው ፕሬዚደንት ዶናልድ ትራምፕ፣ በሩሲያና ዩክሬን መካከል ጦርነቱ ቆሞ በአፋጣኝ ድርድር እንዲጀመር ሁለቱም አገራት መስማማታቸውን አስታወቁ፡፡
ትራምፕ ከሰሞኑ ከሩሲያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ጋር ባደረጉት የ1 ሰዓት ከ30 ደቂቃ የስልክ ንግግር፤ ለሦስት አመት ገደማ የዘለቀውን የሩሲያና ዩክሬን ጦርነት ለማስቆም፣ በአፋጣኝ ድርድር እንዲጀመር መስማማታቸውን ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ተናግረዋል፡፡
ለዚህም ዓላማ በቅርቡ ከፕሬዚዳንት ፑቲን ጋር በሳኡዲ አረቢያ ተገናኝተው እንደሚወያዩ የገለጹት ዶናልድ ትራምፕ፤ በመቀጠልም አንዳቸው የሌላኛቸውን ሀገር ለመጎብኘት ስምምነት ላይ መደረሱን ይፋ አድርገዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ትራምፕ የሩሲያና ዩክሬን ጦርነትን ለማስቆም የሚያስፈልጉ ቅድም ሁኔታዎችን ባይጠቅሱም፤ የአሜሪካ መከላከያ ሚኒስትር ፔቴ ሄግዘ፤ የዩክሬን የኔቶ አባልነት ጉዳይ የማይሳካ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ትራምፕ በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት አሸንፈው ዋይት ሃውስ ከገቡ የዩክሬንና ሩሲያ ጦርነትን እንደሚያስቆሙ ቃል መግባታቸው የሚታወስ ነው፡፡
በሌላ ዜና፤ በሩሲያ ለሦስት ዓመታት ታስሮ የቆየው አሜሪካዊ መምህር ማርክ ፎጌል ከትላንት በስቲያ ማክሰኞ ከእስር ተለቆ ለአገሩ አሜሪካ በቅቷል፡፡ ለታጋቹ አሜሪካዊ መምህር ከእስር መፈታት ትራምፕ ከሩሲያው መሪ ጋር የፈጠሩት ግንኙነት ወሳኝ ነበር ተብሏል፡፡
የፕሬዚዳንቱ ተፈራዳሪ ዊትኮፍ በዋይት ሃውስ በሰጡት መግለጫ፤ "ማርክ ፎጌልን ማስፈታት ወሳኝ ነበር፤ በዚህ ረገድ ሩሲያውያን በጣም፣ በጣም ተባባሪ ነበሩ" ብለዋል፡፡
የፎጌል መለቀቅ የፕሬዚዳንት ትራምፕና ፑቲን ግንኙነት ወደፊት እየጠነከረ የሚሄድ መሆኑን የሚያሳይ ነው ያሉት ዋትኮፍ፤ "መልካም ግንኙነት ነበራቸው ብዬ አስባለሁ፤ ይህም መቀጠል አለበት” ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ፕሬዚዳንት ትራምፕ ማርክ ፎጌልን በዋይት ሀውስ ተቀብለው ያነጋገሩ ሲሆን፤ ፎጌል ከሩሲያ እስር ነጻ ያወጡትን ፕሬዚዳንት ትራምፕና ተደራዳሪዎቹን አመስግኗል፡፡
ፎጌል ለጀርባ ህመሙ በህክምና የታዘዘ ማሪዋና ይዞ በመገኘቱ ምክንያት ነበር በሩሲያ ከ2021 ጀምሮ ለእስር የበቃው፡፡ ማርክ ፎጌልን ከእስር በመልቀቋ ሩሲያን እንደሚያደንቁ የተናገሩት ትራምፕ፤ የተደረገውን ድርድር "በጣም ፍትሃዊ" ሲሉ ገልጸውታል፤የስምምነቱን ዝርዝር ባይናገሩም፡፡
አትሌት ፅጌ ድጉማ በፈረንሳይ ሊቪ የዓለም አትሌቲክ የቤት ውስጥ ውድድር አሸናፊ ሆነች
አትሌት ፅጌ ድጉማ በፈረንሳይ ሊቪ የዓለም አትሌቲክ የቤት ውስጥ ውድድር አሸናፊ ሆነች
በፈረንሳይ ሊቪ የዓለም አትሌቲክ የቤት ውስጥ ውድድር በሴቶች 800 ሜትር አትሌት ፅጌ ድጉማ አሸናፊ ሆናለች፡፡
አትሌቷ 1:59.02 በመግባት ውድደሩን ማሸነፏን ከኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፌዴሬሽን የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡
“ሳላዛት” ረዥም ልብወለድ ለገበያ ቀረበ
በአብርሃም ገነት የተጻፈው “ሳላዛት” የተሰኘ ረዥም ልብወለድ መጽሐፍ፤ ሰሞኑን ገበያ ላይ እንደዋለ ደራሲው ለአዲስ አድማስ ገለጸ፡፡
በ500 ብር ለሽያጭ የቀረበው ልብወለድ መጽሐፉ፤ በጃፋርና በሀሁ መጽሐፍ መደብሮች ማግኘት እንደሚቻል ታውቋል፡፡
አብርሃም ገነት በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በሚጽፋቸው ተወዳጅ አጫጭር ልብወለዶቹና ወጎቹም ይታወቃል፡፡
“ሳላዛት” በረዥም ልብወለድ ዘርፍ፣ ለጸሃፊው የበኩር ሥራው እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡
****
"አለማችን ፕላኔታዊ ውሕደት ያስፈልጋታል"
”--ዓለምን በአንድ ፌደሬሽን ማሰባሰብ ግቡ ሰዋዊና ፕላኔታዊ አንድነት ለማምጣት ቢሆንም ውጤቱ ግን ከዚህ ያለፈ ነው። ዓለምን በአንድ ፕላኔታዊ ፌደሬሽን ማሰባሰብ ያስፈለገው ጦርነትን ለማስቀረት፣ ሰላምና ፍትሕን ለማስፈን፣ የምድር አየር ንብረት ለሰው ልጅና ለሌሎችም ፍጡራን ተስማሚ ሆኖ እንዲቀጥል ለማድረግና ስልጣኔን በተለይም የህዋ ስልጣኔን ለማቀላጠፍ ነው። ስለ ህዋ ስልጣኔ በቀጣዩ ሁለንታዊ መድረክ ስለምናወሳ አሁን በዝርዝር አንሄድበትም። አስተዳደርን በተመለከተ ይህ ፌደሬሽን፣ ዓለምን ጠቅልሎ ይዞ የሚገዛ ተደርጎ መታሰብ የለበትም። አሁን በፌደሬሽኑ ስር ያሉ ሀገራትን እውነታ በተግባር ማየት ትችላላችሁ። የፌደሬሽኑ ስልጣን እንደ መከላከያ፣ የህዋ ምርምር፣ አየር ንብረትና የውጭ ግንኙነት ባሉ የተወሰኑ ጉዳዮች ላይ ነው። እነዚህ ጉዳዮች በቁጥር ውስን ቢሆኑም የምድርንና የሰው ልጅን ዕጣ የሚወስኑ ታላላቅ ጉዳዮች ናቸው። እነዚህ ታላላቅ ጉዳዮች ላይ ስኬት ማምጣት የሚቻለው በሀገራት ደረጃ በተበጣጠሰ ሁኔታ ሳይሆን እንደ ፕላኔት በአንድ ማዕከል መሥራት ሲቻል ነው። ከዚህ ውጭ ሀገራቱ ራሳቸውን ነው የሚያስተዳድሩት። ዓለም በሙሉ በፌደሬሽኑ ስትካተት ደግሞ የፌደሬሽኑ የውጭ ግንኙነት ስልጣን ፕላኔቷን ወደ መወከል ይሸጋገራል።”
( ከ”ሳላዛት“ የተቀነጨበ)
***
መጽሐፉ፤ በአዲስ አበባ በጃፋር እና ሀሁ መጽሐፍ መደብሮች፣ እንዲሁም በባሕርዳር አዳነ መፅሐፍ መደብርና በሌሎች የክፍለ ሀገር ከተሞች መፅሐፍ መደብሮችም ይገኛል፡፡
በቀጥታ መግዛት ለምትፈልጉ ባሕር ዳር፡- 0910625217 አዲስ አበባ፡- 091 396 0314 ወይም 091 128 0984 ደዉሎ ማግኘት ይቻላል፡፡