Administrator

Administrator

 በመላው አለም በሚገኙ የተለያዩ አገራት ባለፉት አስር አመታት በድምሩ ከ1 ሺህ በላይ ጋዜጠኞች እንደተገደሉና በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በየዕለቱ በአማካይ አንድ ጋዜጠኛ እንደተገደለ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አስታውቋል፡፡የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የትምህርት የሳይንስና የባህል ተቋም ከሰሞኑ ይፋ ባደረገው መረጃ እንዳለው፣ ጋዜጠኞቹ ዘገባዎችን በሚሰሩበትና ለህዝብ በሚያቀርቡበት ወቅት በስራ ገበታቸው ላይ እያሉ የተገደሉ ናቸው፡፡ባለፉት አስር አመታት በእነዚህ ጋዜጠኞች ላይ ግድያ ከፈጸሙት ሰዎች መካከል 90 በመቶ የሚሆኑት ግድያውን በመፈጸማቸው በህግ ተጠያቂ እንዳልተደረጉና እንዳልተቀጡ ድርጅቱ ባወጣው መረጃ አስታውቋል፡፡በአለማችን የተለያዩ አገራት ግድያን ጨምሮ በጋዜጠኞች ላይ የሚደርሰው ጥቃት እያደገ መጥቷል ያለው ተቋሙ፣ መንግስታት በመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች ላይ ጥቃት እንዲፈጸም የሚገፋፉ የጥላቻ ንግግሮችንና አባባሽ ድርጊቶችን እንዲያቆሙ ጥሪ አቅርቧል፡፡

ከዚህ በፊት ብዙ ጊዜ ብለነዋል፤ ማንም ስላልሰማን ደግመን እንለዋለን ይላል - አንድ የጥንት ታሪክ ፀሐፊ፡፡ የእኛም እንደዚያው ነው፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት ደገኛ ገበሬዎች አብረው ይኖሩ ነበር፡፡ ሳር ቤት ነው ያላቸው፡፡ ደሳሳ ጎጆዎች ናቸው፡፡ በድንገት አንድ ቀን የአንደኛው ገበሬ ቤት ተለወጠ፡፡ ቆርቆሮ ቤት ሆነ፡፡ ጎረቤትየው ደነገጠና፤
“ወዳጄ፤ እንዴት ይሄ ቤትህ ሊለወጥ ቻለ? ምን ተዓምር ተገኘና ነው?”
ገበሬው፤
“አየህ በሬዎቼን ሸጥኳቸውና ታች ቆላ ወርጄ ብረታ ብረት ገዛሁ፡፡ ከዚያ ደጋ አምጥቼ ለቀጥቃጩ፣ ለባለእጁ፣ ማረሻ ለሚፈልገው ገበሬ ሸጥኩ፡፡ ብዙ ብር አገኘሁ፡፡ ቤቴን ለወጥኩ፡፡ አጥሬን ለወጥኩ፡፡ ራሴን ለወጥኩ!”
“በቃ፤ እኔም እንዳንተ አደርጋለሁ” አለና ሄዶ በሬዎቹን ሸጠ፡፡ ከዚያም ገበያ ገብቶ ማጭድ፣ አካፋ፣ ዶማ፣ ማረፊያ፣ ገሶ … ብቻ አለ የሚባል የብረት ግብዓት ገዝቶ፣ ተሸክሞ፣ ወደ ደጋ ዳገቱን ተያያዘው፡፡
ሆኖም ያን ሁሉ ብረት አቅሙ አልችል አለና ዳገቱ ወገብ ላይ ተዝለፍልፎ ወደቀ፡፡ የመንደሩ ሰው በዚያ ሲያልፍ አየውና፤
“አያ እገሌ ምን ሆነህ ነው?”
“ያ ጎረቤቴ ገበሬ ጉድ አርጎኝ ነው!”
“ምን አደረገህ?”
“ንግድ ጀምሬያለሁ ብሎ የንግዱን ጠባይ ነገረኝ፡፡ ባለኝ መሰረት ንግድ ውስጥ ገባሁ”
“ታዲያ እሱ ምን በደለህና ነው ጉድ አደረገኝ የምትለው?”
“ትርፉን ነግሮ መከራውን ሳይነግረኝ!”
***
አያሌ ትርፍ ያስገኛሉ የተባሉ ነገሮች መከራ እንዳላቸው መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ ቀላል የሚመስሉ ግን ውስብስብ የሆኑ፣ ውስብስብ ሆነው የባሰ የሚወሳሰቡ፣ ሳንማርባቸው ያለፉ፣ ተምረንባቸው የተረሱ፣ ጨርሶ ያላጠናናቸው ብዙ ብዙ ቁምነገሮች አሉ፡፡
“ከበሮ በሰው እጅ ያምር
ሲይዙት ይደናገር!” የሚባለው ተረት፣ ለተሿሚዎቹ ሁሉ የማስጠንቀቂያ ደወል ነው! በተለይ ሴት ተሿሚዎች መብዛታቸው አኩሪ የመሆኑን ያህል ኃላፊነታቸውን መወጣታቸው፣ ከሙስና የፀዱ መሆናቸው፣ የፆታ እኩልነትን ማበልፀጋቸው፣ ለበርካታ ሴቶች አርአያ መሆናቸው፣ ከወንዶች ይልቅ ዝርዝር ጉዳይ ላይ የማተኮር ክህሎታቸው (Meticulousness) እጅግ የላቁ ያደርጋቸዋል! ይሄ ቢሳካልን ላሜ ወለደች ነው! ይህን ዕድል እንደ ሌሎች ያመለጡን ዕድሎች እንዳይሆን መትጋት ያስፈልጋል፡፡ የእናቶች ፀጋ በእጃችን ነው፡፡ የህፃናት ፀጋ በእጃችን ነው፡፡ የትምህርት ፀጋ በእጃችን ነው! የሚያስጎመጅ ዕድል ባያመልጠን መልካም ነው! የዲሞክራሲ፣ የፍትህ፣ የተስፋ፣ የራዕይ ጊዜ እየጀመረ ነውና እንጠቀምበት! ለብዙ ዓመታት የጮህንለት የሴቶች አጀንዳ መልካም ጉዞ ይጓዝ ዘንድ የወንዶችም የሴቶችም ጥያቄ አድርገን እንየው፡፡ አለበለዚያ “የማያስተኛ ነገር ነግረውን ተኝተው አደሩ” ይሆንብናል!!

ከ20 በላይ ፊልሞች ለዕይታ ይቀርባሉ

   በተለያዩ የአውሮፓ አገራት የተሰሩና ዓለም አቀፍ ሽልማት ያገኙ ከ20 በላይ ፊልሞች ለእይታ የሚቀርቡበት የአውሮፓ ፊልም ፌስቲቫል የፊታችን ሐሙስ በቫምዳስ መዝናኛ ይከፈታል፡፡ የአውሮፓ አገራት  አምባሳደሮችና የባህል ማዕከላት ዳይሬክተሮች ከትናንት በስቲያ በቫምዳስ የመዝናኛ ማዕከል በሰጡት መግለጫ፤ በፌስቲቫሉ ላይ የኢትዮጵያዊያን አጫጭር ፊልሞች ለእይታ እንደሚቀርቡና የአውሮፓና የኢትዮጵያ ፊልም ሰሪዎች የልምድ ልውውጥ እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል፡፡
በዘንድሮ የፊልም ፌስቲቫል ላይ የቤልጂየም፣ የቼክ ሪፐብሊክ፣ የዴንማርክ፣ የፈረንሳይ፣ የጀርመን፣ የሀንጋሪ፣ የአየርላንድ፣ የአዘርባጃንና የቱርክ ፊልሞች የሚታዩ ሲሆን ፊልሞቹ ዘጋቢ፣ ታሪካዊ፣ ኮሜዲና ድራማ ዘውግ ያላቸው እንደሆነም ተገልጿል፡፡ ፊልሞቹ በየአገራቱ ቋንቋዎች የተሰሩና የእንግሊዝኛ ሰብታይትል ያላቸው ሲሆኑ ለእይታ የሚቀርቡትም በነፃ ነው ተብሏል፡፡
በዚህም መሰረት የፈረንሳዩ “LeBiro” የተሰኘው ፊልም በመክፈቻ ስነ ሥርዓቱ ላይ ሐሙስ ጥቅምት 22 ቀን 2011 ዓ.ም ከምሽቱ 12፡00 ላይ የሚቀርብ ሲሆን ዓርብ ከቀኑ 8፡00 ላይ የኢትዮጵያ አጫጭር ፊልሞች፣ ከቀኑ 10፡30 ደግሞ የስፔይን፣የአውሮፓ ህብረትና የአፍሪካ ህብረት ፊልሞች ለእይታ ሲበቁ የዛሬ ሳምንት ቅዳሜ ከቀኑ 5፡00 ላይ የስውዲን የህፃናት ፕሮግራም፣ ከቀኑ 8፡00 የስሎቫኪያ፣ ከቀኑ 10፡00 የዩናይትድ ኪንግደም እና ከምሽቱ 12፡30 የኔዘርላንድስ ፊልም ለእይታ ይቀርባሉ፡፡ እሁድ ከቀኑ 8፡00 ደግሞ የፖርቹጋል፣ 10፡00 ላይ የኢጣሊያ፣ ምሽት 1፡00 ላይ የጀርመን ፊልሞች ይታያሉ ተብሏል፡፡
በቀጣዩ ሳምንት ሐሙስ ጥቅምት 29 ከቀኑ 10፡00 የቱርክ፣ ምሽት 1፡00 የአዘርባጃን ፊልሞች የሚታዩ ሲሆን ቅዳሜ ህዳር 1 ረፋድ 4፡00 ላይ የሀንጋሪ የህፃናት ፕሮግራም፣ ከቀኑ 8፡00 የቤልጂየም፣ 10፡00 ላይ  የፊንላንድ፣ ምሽት 12፡30 ደግሞ የዴንማርክ ፊልሞች ለእይታ እንደሚበቁ ታውቋል፡፡ እሁድ ህዳር 2 ቀን 2011 ዓ.ም የፌስቲቫሉ መዝጊያ ሲሆን ከቀኑ 8፡00 የአየርላንድ፣ 10፡00 የቼክ ሪፐብሊክ፣ ምሽት 1፡00 ደግሞ የፖላንድ ፊልሞች ታይተው፣ የፌስቲቫሉ መቋጫ እንደሚሆን ታውቋል፡፡  


አፕልና ሳምሰንግ 15 ሚሊዮን ዩሮ ተቀጥተዋል
 
ታዋቂው የኤሌክትሪክ መኪኖች አምራች ኩባንያ ቴስላ እስከ መስከረም በነበሩት ያለፉት 3 ወራት በድምሩ 311.5 ሚሊዮን ዶላር ትርፍ ማግኘቱንና ባለፉት 15 አመታት ታሪኩ ይህን ያህል የሩብ አመት ትርፍ ሲያስመዘግብ ይህ ለሶስተኛ ጊዜው እንደሆነ ኒውዮርክ ታይምስ ዘግቧል፡፡
ኩባንያው ባለፉት ሶስት ወራት  ከበፊቱ በተሻለ ፍጥነት በርከት ያሉ የኤሌክትሪክ መኪኖችን አምርቶ ለደንበኞቹ ማስረከብ መቻሉ ገቢውንና ትርፉን እንዳሳደገለት የጠቆመው ዘገባው፣ የማምረት አቅሙን የበለጠ ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝም አመልክቷል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ የጣሊያን የንግድ ውድድር ባለስልጣን መስሪያ ቤት፣ ወደ ግዛቴ ያስገቧቸውን የተለያዩ አይነት የሞባይል ምርቶቻቸውን ሆን ብለው ቶሎ እንዲደክሙ አድርገዋል በሚል በአፕል ላይ የ10 ሚሊዮን፣ በሳምሰንግ ላይ ደግሞ የ5 ሚሊዮን ዩሮ ቅጣት እንደጣለባቸው ተዘግቧል፡፡
ኩባንያዎቹ ለጣሊያን ገበያ ያቀረቧቸው የተለያዩ አይነት የሞባይል ስልኮች ቶሎ እንዲደክሙና አዝጋሚ እንዲሆኑ በማድረግ፣ ተጠቃሚዎች ሶፍትዌር አፕዴት እንዲያደርጉ ባልገተባ መንገድ ያስገድዳሉ፤ አፕዴቶቹም የስልኮቹን ፍጥነት ይቀንሳል በሚል ቅጣቱ እንደተጣለባቸው ተነግሯል፡፡
የስልኮችን አቅም የሚቀንስ ሶፍትዌር አፕዴት አላቀረብኩም ያለው ሳምሰንግ፤ የቀረበበትን ክስና ቅጣት በመቃወም ይግባኝ እንደሚጠይቅ  ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፤ አፕልም ተመሳሳይ ምላሽ ይሰጣል ተብሎ እንደሚጠበቅ ጠቁሟል፡፡

ዋረን በፌ በ1ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል

የአፍሪካው ቁጥር አንድ ባለጸጋ ናይጀሪያዊው ቢሊየነር አሊኮ ዳንጎቴ፤ ከፍተኛ በጀት መድበው ትርጉም ያለው ስራን በሚያከናውኑ የአለማችን ምርጥ በጎ አድራጊዎች ዝርዝር ውስጥ የ6ኛ ደረጃን መያዛቸውን ኦል አፍሪካን ኒውስ ዘግቧል፡፡
ከፍተኛ ገንዘብ ለበጎ አድራጎት ተግባራት በማዋል የሚታወቁ የአለማችን ግለሰቦችን ዝርዝር ይፋ ያደረገው ሪችቶፒያ የተባለ የእንግሊዝ ተቋም፣ በፋውንዴሽናቸው አማካይነት 1.25 ቢሊዮን ዶላር ለበጎ አድራጎት ተግባራት የመደቡት ዳንጎቴ 6ኛ ደረጃን መያዛቸውን አመልክቷል፡፡
እ.ኤ.አ በ1981 ባቋቋሙት ፋውንዴሽን አማካይነት በርካታ ቁጥር ያላቸው ዜጎችን ተጠቃሚ ያደረጉ የመሰረተ ልማት ግንባታና የበጎ አድራጎት ስራ ሲያከናውኑ የቆዩት የ61 አመቱ ናይጀሪያዊ ቢሊየነር ዳንጎቴ፣ ከአጠቃላይ የተጣራ ሃብታቸው ከስምንት በመቶ በላይ የሚሆነውን ለበጎ አድራጎት ተግባር እንዳዋሉም ዘገባው አመልክቷል፡፡
በተቋሙ የምርጥ በጎ አድራጊዎች ዝርዝር ውስጥ በአንደኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡት አሜሪካዊው ቢሊየነር ዋረን በፌ ሲሆኑ የማይክሮሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስ በሁለተኛነት ይከተላሉ፡፡
እንግሊዛዊቷ ደራሲ ጄ ኬ ሮውሊንግስ በሶስተኛ ደረጃ ላይ ስትቀመጥ፣ አሜሪካዊቷ የቶክ ሾው አቅራቢ ኦፕራ ዊንፍሬይ አራተኛ፣ የቴስላ ኩባንያ ባለቤት ኤለን ሙስክ ደግሞ አምስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡ ሪቻርድ ብራንሰን፣ ማርክ ዙክበርግ፣ ጄፍ ቤዞስና ማይክ ብሉምበርግ እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአምስተኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ የያዙ ሌሎች በጎ አድራጊዎች ናቸው፡፡


በመላው አለም በሚገኙ የተለያዩ አገራት የኢንተርኔት ዋጋ ከአቅማቸው በላይ በመሆኑ ሳቢያ አገልግሎቱን መጠቀም ያልቻሉ ሰዎች ቁጥር ከ2.3 ቢሊዮን በላይ መድረሱን አንድ አለማቀፍ የጥናት ሪፖርት አስታውቋል፡፡
አሊያንስ ፎር አፎርዴብል ኢንተርኔት የተባለው ተቋም በ61 የአለማችን አገራት ላይ የሰራውን ጥናት መሰረት አድርጎ ሰሞኑን ይፋ ባደረገው አመታዊ ሪፖርቱ እንዳለው፣ ጥናቱ ከተሰራባቸው አገራት መካከል ከ60 በመቶ በላይ የሚሆኑት ከዜጎች የመክፈል አቅም በላይ የሆነ የኢንተርኔት ዋጋ ተመን ያላቸው ናቸው፡፡
በሁሉም አገራት የአንድ ጊጋ ባይት ኢንተርኔት ክፍያ ዋጋ ከአገራቱ አማካይ ወርሃዊ ገቢ ከ5 በመቶ በላይ እንደሚደርስ የጠቆመው ሪፖርቱ፣ የኢንተርኔት አገልግሎት ክፍያ ውድነት በርካታ ዜጎችን የአገልግሎቱ ተጠቃሚ እንዳይሆኑ ከፍተኛ እንቅፋት መሆኑን ቀጥሏል፡፡ በአለማችን የኢንተርኔት ተጠቃሚዎች ቁጥር እድገት በአመቱ ቅናሽ ማሳየቱን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በ2017 መጨረሻ ላይ የአለማችንን የኢንተርኔት አቅርቦት 50 በመቶ ለማድረስ ያስቀመጠውን ግብ ማሳካት እንዳልተቻለም አመልክቷል፡፡


በየመን ለአመታት የዘለቀው የእርስ በእርስ ግጭትና ጦርነት በዚህ መልኩ የሚቀጥል ከሆነ፣ አገሪቱ በአለማችን የ100 አመታት ታሪክ ውስጥ እጅግ የከፋ ይሆናል ለተባለ የረሃብ አደጋ ልትጋለጥ እንደምትችል ተመድ አስጠንቅቋል፡፡
ዘ ጋርዲያን እንደዘገበው፤በየመን ከፍተኛ ቀውስ እየፈጠረ ያለው ጦርነት መፍትሄ ካልተገኘለትና በሳኡዲ የሚመራው ጥምር ሃይል የአየር ጥቃት መፈጸሙን ከቀጠለ በመጪዎቹ ሶስት ወራት ጊዜ ውስጥ 13 ሚሊዮን ያህል የአገሪቱ ዜጎች የከፋ ረሃብ ሰለባ ሊሆኑ ይችላሉ ሲል የተባበሩት መንግስታት ድርጅት አስጠንቅቋል፡፡
በአገሪቱ ለአመታት የዘለቀው ጦርነትና የእርስ በእርስ ግጭት የሰብዓዊ እርዳታ የሚያቀርቡ አለማቀፍ ተቋማትን እንቅስቃሴ በከፍተኛ ሁኔታ እያስተጓጎለው እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፣ በቀጣይም አለማቀፉ ማህበረሰብ ለችግሩ ትኩረት በመስጠት ርብርብ ካላደረገ በርካታ ዜጎች በተለይ ደግሞ ህጻናት በከፋ ረሃብ ለሞት ሊዳረጉ እንደሚችሉ አስጠንቅቋል፡፡
የሁቲ አማጽያን ከሶስት አመታት በፊት መዲናዋን ሰንዓን ጨምሮ የአገሪቱን አብዛኛውን ክፍል መቆጣጠራቸውን ተከትሎ የመን በከፋ የእርስ በእርስ ግጭትና ጦርነት ውስጥ መግባቷን ያስታወሰው ዘገባው፣ በሳኡዲ የሚመራው ጥምር ሃይልም አለማቀፍ እውቅና የተሰጠውን መንግስት በመደገፍ ከአማጽያኑ ጋር ከፍተኛ ጦርነት ውስጥ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡



የላይቤሪያው ፕሬዚዳንት ጆርጅ ዊሃ በሁሉም የአገሪቱ የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች በክፍያ ሲሰጥ የቆየው ትምህርት በነጻ እንዲሆን መወሰናቸውን ከትናንት በስቲያ ይፋ አድርገዋል፡፡
በአገሪቱ ትልቁ የከፍተኛ ትምህርት ተቋም የሆነውን ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ላይቤሪያን ጨምሮ በአራቱም የመንግስት ዩኒቨርሲቲዎች የመጀመሪያ ዲግሪ ተማሪዎች ሽራፊ ሳንቲም ሳይከፍሉ በነጻ ትምህርታቸውን መከታተል እንደሚችሉ ፕሬዚዳንቱ ባስተላለፉት መልእክት አስታውቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ የክፍያ መቅረት ብስራቱን ያሰሙት በመዲናዋ ሞንሮቪያ በሚገኘው ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ላይቤሪያ በመቶዎች ከሚቆጠሩ የዩኒቨርሲቲው ተማሪዎች ጋር በተገናኙበት አጋጣሚ መሆኑን የዘገበው ቢቢሲ፣ በወቅቱ ተማሪዎቹ በደስታ ምላሽ መስጠታቸውንና በመላ አገሪቱ የሚገኙ በርካታ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችም የፕሬዚዳንቱን ብስራት በደስታ እንደተቀበሉት ጠቁሟል፡፡
ፕሬዚዳንት ዊሃም፤ ትምህርት በነጻ እንዲሰጥ ያሳለፉትን ውሳኔ ሌሎች የአፍሪካ አገራትም በአርአያነት ሊከተሉት እንደሚገባ መናገራቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
በአገሪቱ የዩኒቨርሲቲዎች ክፍያ ከጊዜ ወደ ጊዜ በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉ ተማሪዎችንና ወላጆችን ክፉኛ ሲያስቆጣና አመጽ ሲቀሰቅስ እንደነበር ያስታወሰው የቢቢሲ ዘገባ፣ በቅርቡም የአንድ ክሬዲት አወር ክፍያ በግማሽ ያህል መጨመሩ ተቃውሞ ቀስቅሶ እንደነበር አስታውሷል፡፡



 የኢትዮጵያ አዋላጅ ነርሶች ማህበር 27/ኛውን አመታዊ ጉባኤ Oct/12-13/2018/ በአዲስ አበባ አካሄዶአል፡፡ በጉባኤው ላይም በተለያዩ መስተዳድሮች ባሉ የህክምና ተቋማት የሚያገ ለግሉ አዋላጅ ነርሶች እንዲሁም ከተለያዩ የሚመለከታቸው መስሪያ ቤቶች የተወከሉ ባለሙያዎች ተሳት ፈዋል፡፡ ጉባኤው በሁለት ቀን ቆይታው በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ውይይት ያደረገ ሲሆን በተጨማሪም የምርምር ጽሁፎችም ቀርበው ነበር፡፡ ከቀረቡት የምርምር ጽሁፎች ውስጥ አንዱ በቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ላይ ለተጠቃሚዎች የሚሰጠውን የምክር አገልግሎት ጥራትና ብቃት እን ዲሁም መሻሻል የሚገባቸውን ነገሮች የጠቆመው አንዱ ነበር፡፡ ይህን የምርምር ጽሁፍ ያቀረ ቡት ዶ/ር እውነት ገብረሀና ናቸው፡፡ ጥናቱ የያዛቸውን ቁም ነገሮች እንደሚከ ተለው ለንባብ ብለናል፡፡
የቤተሰብ እቅድ ዘዴን የምክር አገልግሎት በሚመለከት በኢትዮጵያ፤ በሜክ ሲኮና በህንድ ጥራቱን የጠበቀ እና ተገቢውን አገልግሎት ለመስጠት የሚያስችል መረጃን በሚፈ ለገው ደረጃ ለመስጠት እንዲቻል ለማድረግ የተሰራ ጥናት ነው፡፡ ይህንን ጥራቱን የጠበቀ የምክር አገ ልግ ሎት በሚመለከት አገልግሎት በሚሰጥባቸው አንዳንድ አካባቢዎች ዳሰሳ መደረጉን መረ ጃው ይጠቁማል፡፡
በኢትዮጵያ የጤናው አገልግሎትን በጥራትና በእኩል የማዳረስ ተግባር በጤናው የልማት እቅድ ውስጥ ከተነደፉት እቅዶች ዋነኛው ግብ ተደርጎ የሚወሰድ ነው፡፡ የኢፊድሪ ጤና ጥበቃ ሚኒስ ቴር በነደፈው ብሔራዊ አጀንዳ ውስጥ የጥራት ተግባር አንዱ ሲሆን  ጥራትንም ማሻሻል ሌላው በትኩረት እየተሰራበት ያለ ጉዳይ ነው፡፡ ስለዚህም ይህ ጥናት ለሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የጥ ራት ማሻሻል ፕሮግራም አስተዋጽኦ ያደርጋል በሚል እንደሚታመን ዶ/ር እውነት ገ/ሐና ገልጸዋል፡፡
ይህ ጥናት በተለይም ሴቶች በቤተሰብ እቅድ ዘዴ አገልግሎት የምክር አሰጣጥ ላይ ምን ልምድ አላቸው? የሚለውን ከተጠቃሚዎች ለማወቅ ሙከራ አድርጎአል። ለዚህም በአዲስ አበባ በጉለሌ ክፍለ ከተማ በሚገኙ /4/የጤና ጣቢያዎች እንዲሁም /8/ የሚሆኑ የቡድን ውይይቶች /52/የቤ ተሰብ እቅድ ዘዴ ተጠቃሚ ሴቶች እንዲሁም በጉዳዩ ዙሪያ ቀደም ሲል ከተደረጉ የዳሰሳ ጥና ቶች የተፈተሸ ሲሆን ውጤቱም እንደሚከተለው ነው፡፡
በጥናቱ እንደተገኘው እውነታ ብዙ ሴቶች አገልግሎቱን የሚሰጡ ባለሙያዎች የሚሰጡትን ምክር እና ጥቆማ በቀላሉ የሚቀበሉ ወይንም የሚያምኑ ሲሆን ሌሎቹ ደግሞ የበለጠ እውቀት አላቸው ብለው የሚያምኑት በቀጥታ እነሱ ያገኙዋቸውን የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ሰጪ ዎችን ሆኖ ተገኝቶአል፡፡
አገልግሎት ሰጪዎች ተገልጋዮቻቸውን እንዲያዳምጡ፤ ክብር እንዲሰጡ፤ የተገልጋዮችን የግል ምስጢርን እንዲጠብቁ እና እምነት እንዲጣልባቸው እንዲሁም ከደንበኛቸው የሚነገራቸውን በጥንቃቄ እንዲያደምጡ እና እንዲተገብሩ እንደሚፈለግ ከተገልጋዮች የተገኙ ምስክርነቶች ያረጋግጣሉ። ብዙ ሴቶች እንደተናገሩትም ‹‹…አገልግሎት ሰጪዎች የሚናገሩትን እንድንሰማ ብቻ ሳይሆን እንዲ ያውም ጥያቄ እንድንጠይቅና የምናውቀውን ወይንም የምናምንበትን ነገር እንድንናገር እንዲያበረታቱ ይጠበቅባቸዋል…›› ብለዋል።
ጥናቱ እንደደረሰበት ከሆነ አንዳንድ ሴቶች ካለምርጫቸው ያልተፈለገ እርግዝና መከላከያውን እንዲወስዱ በአገልግሎት ሰጪዎች ግፊት እንደሚደረግባቸው እና ይህም እምነት እንዲያጡ የሚያ ስችል ድርጊት በመሆኑ ምናልባትም ሴቶች ተመልሰው ወደ አገልግሎት መስጫው እንዳይሄዱ ሊያደርጋቸው እንደሚችል ይገመታል፡፡
የቤተሰብ ምጣኔ አገልግሎት ላይ የሚሰጠው የምክር አገልግሎት የተገልጋይዋን የግል መብት እና በራስ የመተማመን ሁኔታዋን የማያበላሽ እና የተከበረ እንዲሆን ተገልጋዮች ይፈልጋሉ፡፡ ደንበኞች የግል መብታቸው ካልተከበረ በተቃራኒው መናገር ወይንም የመናደድ ሁኔታ ሊያሳዩ እና የአገልግሎት መሰኩን ወዳለማክበር ሊሸጋገሩ እንደሚችሉ ማወቅ ለአገልግሎት ሰጪው ይጠቅማል፡፡
አብዛኞቹ የቤተሰብ እቅድ ዘዴ ተገልጋዮች አገልግሎት ሰጪዎቹ ከተገልጋይ ጋር ሲገናኙ በሚ ኖረው መግባባት ወይንም መነጋገር በሚያስፈልግበት ጊዜ የበለጠ እድል ወይንም ኃይል እንዳ ላቸው ያምናሉ፡፡እንደነዚህ አይነት ሴቶች አገልግሎቱን ለማግኘት በሚኖረው ማንኛውም ድርጊት በትእግስት መጠበቅን ይመርጣሉ፡፡ ለምሳሌም ብዙ ሰአት መጠበቅ ወይንም በአገል ግሎት አሰ ጣጡ ጎደሎ ነገር ቢመለከቱም በትእግስት ሁኔታውን ከመከታተል ውጪ ምንም እርምጃ አይወስዱም ወይንም ጥያቄ አይጠይቁም፡፡
በጥናቱ ከተመለከተው እና ለጥራት አጋዥ ከተባሉት ውስጥ መረጃን የሚመለከት ይገኝበታል፡፡ ከአንዳንድ ተገልጋዮች እንደተገኘው እማኝነት ከሆነ የተለያዩ ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችሉ አገልግሎቶችን ከራሳቸው ምርጫ ውጪ መውሰድ እንደሚችሉ እንደተነገራቸው ይገልጻሉ፡፡ የመከላከያ አይነቶቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡
በክንድ ውስጥ የሚቀበር (NorPlant)
ሉፕ በመባል የሚታወቀው (IUD)
በመርፌ መልክ የሚወሰድ
በኪኒን መልክ የሚወሰድ ነው፡፡
የምክር አገልግሎት ሰጪዎቹ የእያንዳንዱን መከላከያ ዘዴ ጥቅም እና ጉዳት በሚመለከት መረጃ ለተገልጋዮቹ የሚሰጡ ሲሆን አንዳንድ ጊዜ ግን ተገልጋዮቹ ምንም ማብራሪያ ሳይሰ ጣቸው እራሳቸው የመሰላቸውን ወይንም የፈለጉትን ለመውሰድ ወስነው መጠቀም እንደሚ ጀምሩ ተናግረዋል፡፡  
የምክር አገልግሎቱን በሚመለከት ተጠቃሚዎች እንደመሰከሩት የሚነገራቸው ትእዛዛዊ በሆነ መልኩ ይሔንኛው ቢወሰድ ይሻላል በሚል አይነት ሲሆን ለዚህም በክንድ ውስጥ የሚቀበርና ሉፕ የተሰኘውን ዘዴ እንዲመርጡ እንደሚያደርጉዋቸው ይናገራሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ መርፌ ውንና በኪኒን መልክ የሚወሰደውን ጤናማ እንዳልሆኑና ብዙ ተያያዥ የሆኑ ችግሮችን እንደ ሚያስከትል የሚናገሩ የምክር አገልግሎት ሰጪዎች እንዳሉ ጠቁመዋል፡፡
…አንዲት ሴት ከወለደች በሁዋላ በተሰጣት የምክር አገልግሎት ሉፕ የተሰኘውን የመከላከያ ዘዴ ብትወስድ እንደሚሻላት ስለተነገራት እሱዋም እንዲያውም በየጊዜው ወደጤና ተቋሙ እንዳትመላለስ እንደሚረዳት በማመን እንደተቀበለችው ተናግራለች፡፡
በተለያዩ ስፍራዎች ያሉ አማካሪዎች ከሚሰጡት ምክር በመነሳት ሴቶች የአጭር ጊዜ ያልተ ፈለገ እርግዝና መከላከያን ማግኘት እንደማይችሉ አንዳንዴም አቅርቦት እንደማይኖር የመሳሰ ለው ምክንያት ሁሉ ስለሚነገራቸው ብዙዎች ሴቶች ካለምርጫቸው ለረጅም ጊዜ መከላከያ እንደ ተጋለጡ በጥናቱ ግንዛቤ ተወስዶአል፡፡   
አንዲት የ24/አመት እድሜ ያላት ወጣት የሚከተለውን ምስክርነት ሰጥታለች፡፡
‹‹….በመርፌ የሚወሰደውን መከላከያ መውሰድ እፈልጋለሁ ስላቸው እነርሱ ግን እኔ እንድ ወስድ የመረጡት ሉፕ የተሰኘውን ነበር፡፡ እኔ እንደምገምተው …ተገልጋዩ በየጊዜው እየሄደ እንዳያሰለቻቸው የረጅም ጊዜውን ሰጥተው ለመገላገል ያሰቡ ይመስለኛል፡፡እነርሱ የመረጡትን መከላከያ እኔ አላውቀውም፡፡ ወደፊት ምን ጉዳት እንደሚኖረው ምንም ሀሳብ የለኝም፡፡ …›› ነበር ያለችው፡፡
የጥናቱ መደምደሚያ የሚያዘነብለው የተገልጋዮችን ፍላጎት ማስቀደም ይገባል ወደሚለው ነው፡፡ በእርግጥ ብዙ ሴቶች በምክር አገልግሎቱ በተገቢው መንገድ ተገልግለናል ቢሉም በምክር አገል ግሎት አሰጣጡ ምንም አልረካንም ያሉም ቀላል ቁጥር የላቸውም፡፡
ሴቶች ለሚያነሱዋቸው ጥያቄዎች ተገቢው መልስ አይሰጥም፤
የሚወሰደውን መከላከያ በሚመለከት ስላለው ባህርይ ሙሉ መረጃ አለመስጠት፤
በአማራጭ ሊወሰድ ስለሚችለው የመከላከያ ዘዴ መረጃን አለመስጠት…ወዘተ
ጥናቱ በማጠቃለያው የጠቆመው የቤተሰብ እቅድ ዘዴ የምክር አገልግሎት ሰጪዎች ለተገል ጋዮች ከፍተኛ የሆነ ክብር የሚሰጡ እና እምነት የሚጣልባቸው ከሆኑ ጥራት ላለው የቤተሰብ እቅድ ዘዴ ምክር አገልግሎት አሰጣጥ መሰረት ይሆናል፡፡
የምክር አገልግሎት አሰጣጡ ደንበኞች ስለአገልግቱ ተገቢውን መረጃ እንዲያገኙ በማድረግ እና ባጠቃላይም ተገልጋዩን ያማከለ ቢሆን ጥራት ያለው የምክር አገልግሎት መስጠት ያስችላል… ውጤቱም ይሰምራል ሲል በዶ/ር እውነት ገ/ሐና የቀረበው ጥናት መረጃውን ያጠቃል ላል፡፡

Sunday, 28 October 2018 00:00

“ወርደን እናየዋለን!”

ከዕለታት አንድ ቀን ሁለት ጎረቤታም ገበሬዎች ስለሚዘሩት እህል ይመካከራሉ፡፡
አንደኛው -
“ዘንድሮ ምን ብንዘራ ይሻላል?”
ሁለተኛው -
“በቆሎ ብንዘራስ?”
አንደኛው -
“አዬ በቆሎ አይሆንም፡፡ በቆሎ በቀላሉ በእንስሳቱ ስለሚጫር አያስተርፉልንም፡፡”
ሁለተኛው -
“እንግዲያው ባቄላ ይሁና?”
አንደኛው -
“አዬ እሱማ አልሸሹም ዞር አሉ ነው”
ሁለተኛው -
“ካልሆነ ማሽላ ይሁና?”
አንደኛው -
“ማሽላ ደግሞ ገና ከመሬት ብቅ ሳይል የወማይ ወፍ መጫወቻ መሆኑ ነው፡፡”
ሁለተኛው -
“አሁን እኛን በጣም የሚያስፈራን እህሉ ከመሬት ብቅ ሳይል ተጭሮ መበላቱ ነው እንጂ ከበቀለማ በኋላ ጠባቂ እናስቀምጥለታለን፡፡”
አንደኛው -
“ይልቅ አንድ ዘዴ ታየኝ”
ሁለተኛው -
“ምን ታየህ?”
አንደኛው
“ወጣም ወረደ የሚያስቸግሩን ዝንጀሮና ጦጣ ከሆኑ፣ መንገዳችን ላይ አንዳቸውን ማግኘታችን አይቀርም፡፡ ያልዘራነውንና ለእነሱ የማይመቻቸውን እህል ጠቅሰን ለምን አናታልላቸውም?”
ሁለተኛው -
“በጣም ድንቅ መላ ነው”
በዚህ ተስማምተው በቆሎ ዘርተው ሲመለሱ፣ ጦጢት ዛፍ ላይ ሆና አገኙዋት፡፡
ጦጢት
“አያ ገበሬ?”
ገበሬ
“እንዴት ከርመሻል ጦጢት?”
ጦጢት
“ዘንድሮ ምን ዘርተህ መጣህ?”
ገበሬ -
“ተልባ፡፡ ተልባ ዘርቼ መጣሁ፡፡”
ገበሩው ይሄን ያለው ጦጣ ተልባ ጭራ ማውጣት እንደማትችል ስለሚያውቅ ነው፡፡
ጦጢትም፤
“ይሁን፡፡ ወርደን እናየዋለን!” አለችው፡፡
***
እኛ ስለ ሌሎች ደካማ ጎን ስናስብ፣ እነሱስ ስለኛ ደካማ ጎን ምን ያስባሉ? ብሎ ማሰብ ከብዙ ስህተት ያድነናል፡፡ አስቀድሞ ነገር በሌሎች ደካማ ጎን በመጠቀም ዕድገትን ማሰብ ተላላነት ነው፡፡ “እዛም ቤት እሳት አለ” የሚለውን ተረት ማጤን እጅግ ተገቢ የሆነበት ወቅት ላይ መሆናችንን እናስተውል፡፡ ክልልና ክልል፣ ፓርቲና ፓርቲ፣ ድርጅትና ድርጅት፣ ቡድንና ቡድን ቀና ውድድር ቢያደርጉ እንጂ በመሻኮትም ሆነ በመጠላለፍ ከቶም ትርፍ አያገኙም፡፡ ቀና ያልሆነውን መንገድ ለዘመናት እንደማያዋጣን አይተነዋል፡፡ በጠረጴዛ ውይይት ካልሆነ የማይፈቱ አያሌ ችግሮች እንዳሉብን እየታወቀ፤ መልሰን ግጭትና ሴራ ውስጥ መዘፈቅ ውሃ ወቀጣ ከመሆን አይዘልም፡፡
“እኛ ሳንስማማ
እኛ እየተባላን
መቼም ሳንቻቻል
እንኳን ሰማዩና መሬቱም ይርቃል!”
ስለ ሰላም እያወራን፣ ስለ ፍቅር እየሰበክን፣ ስለ እርቅ እያወሳን ወዘተ … መልሰን ከተጋጨን የተጫረው ብርሃን ይጨለመለማል፡፡ የለኮስነው ቀንዲል ይጠፋል፡፡ ያቀድነው ዲሞክራሲ፣ እናጠራዋለን ያልነው ፍትህ ሁሉ
“ወጣ ወጣና እንደሸምበቆ፣ ተንከባለለ እንደሙቀጫ” ይሆንብናል፡፡
ምንም እንኳ የተያያዝነው የለውጥ ሂደት ዕድሜው አጭር ቢሆን፣ ገና ዳዴ እያልን ነው ብለን ስህተት እያየን እንደ ፍጥርጥሩ ማለት አንችልም፡፡ ባወጣ ያውጣው ብለን ጥፋትን ሳንዳኝ፣ ችግርን በሰዓቱ ሳንፈታ መጓዝ “ሃማሊያን በሁለት ቆራጣ እግር” እንደሚባለው ይሆንብናል፡፡ ገና ብዙ ዳገት እየጠበቀን ሜዳው ላይ ከደከምን “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” ይሆናል፡፡ ከውጪው ዓለም ጋር ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነትና ኢኮኖሚያዊ ስምምነት መፈራረማችን በጎ ጎናችን የሆነውን ያህል፤ የውስጥ ችግራችንን በወቅቱ አለመፍታት አገርን ስጋት ላይ መጣል ነው፡፡ ችግራችን ከላይ ከላይ እንደሚወራውና የሚለባበስ ነገር አይደለም፡፡ ግልጥ ያለና አስጊ ነው፡፡ እንደ ጦጣዋ “ወርደን እናየዋለን” ማለት ዞሮ ዞሮ ጥቅሙ ለእኛው ነውና፣ መሬት የረገጠ ነገር እንሥራ፡፡
ዛሬም፤
“… ከውጪ ያለውን ሄዶ ከመፈለግ
ከውስጥ ያበራውን እንዲወጣ ማድረግ” ብንል ይሻላል!
ልዩ ልዩ ሹመቶች እየተሰጡና ተቋማት እየተጠናከሩ መሆኑ ደግ ነገር ነው፡፡ ሹመኞች ኃላፊነታቸውን ይወጣሉ አይወጡም የሚለው መለኪያው ጊዜ ቢሆንም ቢያንስ ሙስና ውስጥ አይዘፈቁም የሚል ዕምነት አለን፡፡ ተስፋችን ትልቅ ነው፤ ጉዞው ጠመዝማዛ ነው - ጥናቱን ይስጣችሁ ማለት የአባት ነው!