Administrator

Administrator

  ደራሲ የኑስ በሪሁን ያዘጋጀው “በእርግጠኝነት መለሰኝ” የተሰኘ መፅሀፍ የፊታችን ሁሙስ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በአዜማን ሆቴል ይመረቃል፡፡
በልብ ወለድ አተራረክ ስልት የተቃኘውና ታሪክንና ነባራዊ ሁኔታን ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ያለፈውን ከአሁን እያጠቀሰ የሚቃኘው መፅሃፉ፤ መቼቱን በሰሜኑ የአገራችን ክፍል በሚገኝ ትልቅ ከተማ የትምህርት ተቋም ላይ ያደረገ ሲሆን ሁነቶችን እያሰናሰለ ለውጥ የሚፈጥር መፅሀፍ መሆኑን ደራሲው በመግቢያቸው አስፍሯል፡፡ በ317 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ120 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ በምርቃት ስነስርዓቱ በመፅሀፉ ላይ ዳሰሳ የሚካሄድ ሲሆን የተለያዩ ኪነ-ጥበባዊ ዝግጅቶች ይካሄዳሉም ተብሏል፡፡

 የቀድሞው አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት) ከፍተኛ አመራር የነበሩት የኢ/ር ዘለቀ ረዲ፤ “የ21ኛው ክፍለ ዘመን መሳፍንትና ኢትዮጵያን እንደ ሀገር የማስቀጠል ፈተና” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ መፅሃፉ  መሳፍንታዊ አስተሳሰብ ከጥንት ጀምሮ በአገሪቱ ላይ ስላስከተለው ጉዳት፣ አሁን ድረስ የዘለቀው ይህ አስተሳሰብ እንዴት ከፋፍሎ እንደሚገዛ፣ አስተሳሰቡ ህዝቡን ከፋፍሎ ስለሚገዛባቸው መሳሪያዎች፣ በአስተሳሰቡ የትኛው የህብረተሰብ ክፍል ሰለባ እንደሆነና እንዴት ስር ሰዶ አሁን እስካለንበት ዘመን እንደመጣ ይተነትናል፡፡
መሳፍንታዊ አስተሳሰብ አገሪቱን እንደ አገር ለማስቀጠል ምን ያህል ፈተና እንደሆነ የሚገልፀው መፅሃፉ፤ ይህን አስተሳሰብ ከስሩ ለመንቀል የሚያስችሉ የመፍትሄ ሀሳቦችን ይጠቁማል፡፡  በ14 ምዕራፎች  በ236 ገፆች የተመጠነው መፅሀፉ፤ በ75 ብር ከ99 ሳንቲም እና በ28 ዶላር ለገበያ የቀረበ ሲሆን ሎሚ ቡክስ በተባለ የኦላይን የመፅሀፍ ገበያም ጭምር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡

Sunday, 10 September 2017 00:00

በዳይመንድ ሊግ

 • ዘንድሮ የኬንያ አትሌቶች ድርሻ ከ740.5 ሺ ዶላር በላይ ሲሆን የኢትዮጵያ አትሌቶች ድርሻ እስከ 198ሺ ዶላር ነው፡፡
                      • በ2017 ኬንያ 4 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች ኢትዮጵያ ምንም
                      • ባለፉት 8 የውድድር ዘመናት ኬንያ 37 ኢትዮጵያ 12 የዳይመንድ ሊግ ድሎች
                   
       ዳይመንድ ሊግ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች የሚዘጋጅ ሲሆን ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ከሚያቀርቡ የማራቶን ውድድሮች ቀጥሎ ለአትሌቶች ከፍተኛ የገቢ ምንጭ የሆነና በከፍተኛ እድገት ላይ የሚገኝ ዓመታዊ ውድድር ነው፡፡ ዳይመንድ ሊግ ዘንድሮ ለ8ኛ ጊዜ ሲካሄድ በአዲስ መዋቅር  ሲሆን በ32 የውድድር መደቦች በሁለቱም ፆታዎች 1200 አትሌቶች ተሳትፈውበታል፡፡ ትራክ ስታት www.track-stats.com የተባለ ድረገፅ በሰራው ስሌት  በ8ኛው የዳይመንድ ሊግ ላይ  ከቀረበው 8 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ሽልማት 607 አትሌቶች ከ1ሺ ዶላር ጀምሮ እስከ 134ሺ ዶላር ተሸልመዋል፡፡ ዘንድሮ በዳይመንድ ሊጉ ከፍተኛውን የገንዘብ ሽልማት በመውሰድ አንደኛ ደረጃ የተሰጣት 134ሺ ዶላር ማሸነፍ የቻለችው  ኤለና ቶምሰን ከጃማይካ ስትሆን፤ ሽዋኔ ሚለር ከባህማስ በ127ሺ ዶላር፤ ማርያ ላስቲስኤኔ ከራሽያ በ100ሺ ዶላር እንዲሁም ሙታዝ ኡሳ ከቦትስዋና በ100ሺ ዶላር እስከ አምስተኛ ደረጃ አከታትለው ወስደዋል፡፡ ከኬንያ ኤለን ኦቡሪ፤ ከደቡብ አፍሪካ ካስተር ሴማንያ፤ ከቦትስዋና ኒጄል አሞስ፤ ከአሜሪካ ሽዋን ሄንድሪክስ፤ ከግሪክ ካተሪን ሴፈንዲ በነፍስ ወከፍ 90ሺ ዶላር እንዲሁም ከክሮሽያ ሳንድራ ፔርኮቪች 86ሺ ዶላር ከሽልማት ገንዘቡ በመቋደስ እስከ 10ኛ ደረጃ ለማግኘት ችለዋል፡፡
በሌላ በኩል በ8ኛው ዳይመንድ ሊግ በቅርብ ተቀናቃኞቹ የኬንያ እና ኢትዮጵያ አትሌቶች መካከል ከሽልማት ገንዘቡ በተገኘ ድርሻ ከፍተኛ ልዩነት ተስተውሏል፡፡ የትራክ ስታት የሽልማት ገንዘብ ስሌት እንዳመለከተው ኬንያውያን ከ1 እስከ 10፤ ከዚያም እስከ 20 እንዲሁም እስከ ሃምሳኛ እና እስከ መጨረሻው ደረጃ በርካታ አትሌቶችን በማሳተፍ ከገንዘብ ሽልማቱ በ3 እጥፍ ከኢትዮጵያ የሚልቅ  ድርሻ በማግኘት ተሳክቶላቸዋል፡፡ በአጠቃላይ በዳይመንድ ሊጉ ላይ ዘንድሮ ኬንያ 49 አትሌቶችን በማሳተፍ ከ740.5ሺ ዶላር በላይ ስትሰበስብ አራት የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች አግኝታለች፡፡ ከ7 የውድድር ዘመናት በኋላ የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮን ሳታስመዘግብ የቀረችው ኢትዮጵያ 19 አትሌቶችን በማሳተፍ ከሽልማት ገንዘቡ ያስመዘገበችው ድርሻ 148ሺ ዶላር ብቻ ሆኗል፡፡  የኢትዮጵያ አትሌቶች ከዳይመንድ ሊጉ የሽልማት ገንዘብ የሚኖራቸው ድርሻ የቀነሰው በዓለም ሻምፒዮና ተሳትፎ ሳቢያ አትሌቶች ከውድድር ተሳትፎ በመታገዳቸው፤ በምርጥ አሰልጣኞች እና በቂ የልምምድ ጊዜ ባለመስራታቸው፤ በውስን የውድድር መደቦች በሁለቱም ፆታዎች በመሳተፋቸው እና በተቃናቃኝ አትሌቶች የውድድር ታክቲክ እና ቴክኒክ በመበለጣቸው ነው፡፡ የኬንያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን የአትሌቶችን የዳይመንድ ሊግ ተሳትፎ ባለማገዱ እንዲሁም ከኢትዮጵያ በተሻለ የውድድር መደቦች በብዛት መሳተፋቸው ከሽልማት ገንዘብ ያገኙትን ድርሻ የላቀ አድርጎታል፡፡
በትራክ ስታት www.track-stats.com ስሌት መሰረት ከኢትዮጵያ አትሌቶች ግንባር ቀደም ሆኖ የሚጠቀሰው በ5ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ሙክታር ኢድሪስ በ42ሺ ዶላር የሽልማት ድርሻው ከዓለም 49ኛ ደረጃ በማግኘቱ ነው፡፡  ዮሚፍ ቀጀልቻ በ24ሺ ዶላር 93ኛ፤ ዳዊት ስዩም እና በሱ ሳዶ በ16ሺ ዶላር 136ኛ እና 137ኛ፤ ጉድፍ ፀጋይ በ15.5 ሺ ዶላር 142ኛ ላይ ናቸው፡፡ ሌሎች የኢትዮጵያ አትሌቶች ከ150ኛ በታች  እስከ 350ኛ ደረጃ ተዘበራርቀው ሊቀመጡ በቅተዋል፡፡ አማን ወጤ 13፤ ሶፍያ አሰፋ 13ሺ፤ ሃብታም አለሙ 12፤ ሰለሞን ባረጋ 12፤ ለተሰንበት ግደይ 11፤ የኔው አላምረው 8፤ በሱ ሳዶ 5.5፤ ገንዘቤ ዲባባ፤ 4.5፤ እቴነሽ ዲሮ 4.5፤ ጫላ ባዬ 3ሺ፤ ብርሃኑ ለገሰ 2.5፤ ስንታየሁ 1.5፤ ዳዊት ወልዱ 1.5 እንዲሁም ሰለሞን በልሁ 1ሺ ዶላር ከ8ኛው የዳይመንድ ሊግ የገንዘብ ሽልማት አግኝተዋል፡፡
ዳይመንድ ሊግ ከ1998 እኤአ እስከ 2010 እኤአ ለ11 የውድድር ዘመናት ይካሄድ የነበረውን የአይኤኤፍ ጎልደን ሊግ በተሻለ ደረጃ የተካ ነው፡፡ ለ12 የውድድር ዘመናት የተካሄደው ጎልደን ሊግ በ6 ከተሞች በሚደረጉ ውድድሮች የሚያሸንፉ አትሌቶችን 1 ሚሊዮን ዶላር ወይንም የወርቅ ጡቦች በማካፈል የሚሸለምበት ነበር። በጎልደን ሊግ በ1998 እኤአ ላይ ኃይሌ ገብረስላሴ 333,333 ዶላር፤ በ2006 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ በነፍስ ወከፍ 83,333 ዶላር እንዲሁም ቀነኒሳ በቀለ በ2009 እኤአ ላይ 333,333 ዶላር ተሸላሚዎች ነበሩ፡፡
የጎልደን ሊግ ውድድርን የተካው ዳይመንድ ሊግ  ባለፉት 8 የውድድር ዘመናት ከፍተኛ ለውጥ እና ድምቀት በማሳየት ከአይኤኤኤፍ ውድድሮች ስኬታማው ሆኖ እየተጠቀሰ ይገኛል፡፡ ዳይመንድ ሊጉ በየሚካሄድባቸው ከተማዎች ከፍተኛ የስታድዬም ተመልካች አለው። በተለይ በአሜሪካ ዩጂን፤ በስዊዘርላንድ ዙሪክ፤ በሞናኮ  እንዲሁም በእንግሊዝ በርሚንግሃም ከተሞች የሚካሄዱት የዳይመንድ ሊግ ውድድሮች ስታድዬም በሚገባ ተመልካች እየገዘፉ ናቸው፡፡ በቴሌቭዥ ስርጭት ከፍተኛውን ሽፋን በማግኘት ከአትሌቲክስ ውድድሮች ዋና ተጠቃሽ የሆነው ዳይመንድ ሊግ  የዓለም መገናኛ ብዙሃንን ትኩረት በመሳብ ውጤታማም ነው፡፡ በዳይመንድ ሊጉ የየአገራቱ ምርጥ አትሌቶች፤ የዓለምና የኦሎምፒክ ሻምፒዮኖችን መሳተፋቸው ምርጥ ፉክክር የሚስተዋልበት መድረክ አድርጎታል፡፡ ካለፉት ሁለት የውድድር ዘመናት ወዲህ በ4 አህጉራት ኤስያ፤ አውሮፓ፤ መካከለኛው ምስራቅ፤ አሜሪካን እንዲሁም አፍሪካን በማካለል የሚካሄደው ዳይመንድ ሊጉ በ4 ወራት  በ13 የተለያዩ አገራትና 15 ከተሞች ሲስተናገድ  በከፍተኛ የውድድር ደረጃው ሪከርዶች እና የውድድር ዘመኑ ፈጣን ሰዓቶች የሚመዘገቡበት ታላቅ መድረክ እየሆነ መጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ባለፉት ስምንት የውድድር ዘመናት በዳይመንድ ሊጉ ተግባራዊ የሆኑ አዳዲስ የአሰራር መዋቅሮች በሻምፒዮናው የእድገት ደረጃ ፈጣን ለውጥ እንዲመዘገብ ምክንያት ሆነዋል፡፡ በዳይመንድ ሊጉ የአሰራር መዋቅር ለውጦች የተደረጉት ለ3 ጊዜያት ነው፡፡ በመጀመርያዎቹ 6 የውድድር ዘመናት በ12 ከተሞች ውድድሮች እየተካሄዱ ከ1 እሰከ 3 ለሚወጡ አትሌቶች ብቻ   አሸናፊዎችን ለመለየት  ነጥብ በመስጠት በውድድር ዘመኑ መጨረሻ ከፍተኛውን ነጥብ ለሚያስመዘግቡት ሻምፒዮንነቱ ይፀድቅ ነበር።  በ2016 እኤአ በ7ኛው የውድድር ዘመን በተመሳሳይ ሻምፒዮኖችን በከፍተኛ ነጥብ የመለያ መንገድ ከ1 እሰከ 6ኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች ነጥብ በመስጠት ተሰርቶበታል፡፡ በ2017 እኤአ ላይ ግን የአሰራር መዋቅሩ በጣም ልዩ ለውጥ ተደርጎበታል፡፡ በመጀመርያ 12 የማጣርያ ውድድሮች የተካሄዱ ሲሆን ከ1 እስከ 8ኛ ደረጃ ለሚያገኙት ነጥብ  ተሰጥቶ የዳይመንድ ሊጉ አሸናፊዎች የሚለዩት በሁለት ከተሞች በሚከናወኑ የፍፃሜ ውድድሮች ሆኗል፡፡ 12ቱን የዳይመንድ ሊግ የማጣርያ ውድድሮች ዘንድሮ ያስተናግዱት የዶሃ ከተማ በኳታር፤ የሻንጋይ ከተማ በቻይና፤ የዩጂን ከተማ  በአሜሪካ፤ የሮም ከተማ  በጣሊያን፤ የኦስሎ ከተማ በኖርዌይ፤ የቶክሆልም ከተማ በስዊድን የፓሪስ ከተማ በፈረንሳይ፤ የዙሪክ ከተማ በስዊዘርላንድ፤ የበርሚንግሃም ከተማ በእንግሊዝ፤ የራባት ከተማ በሞሮኮ ፤ የሞናኮ ከተማ በሞናኮ እንዲሁም የለንደን ከተማ በእንግሊዝ  ናቸው። ከእነዚህ የ12 ከተሞች የማጣርያ ውድድሮች በኋላ በከፍተኛ ነጥብ በየውድድር መደቡ የጨረሱ አትሌቶች የዳይመንድ ሊጉ ሻምፒዮኖች በሚለዩት በስዊዘርላንድ ዙሪክ እና በቤልጅዬም ብራሰልስ የሚካሄዱ ውድድሮች ተለይተዋል፡፡
ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ዘንድሮ በዳይመንድ ሊግ ለማጣርያው እና ለፍፃሜ ውድድሮች ያቀረባቸው የተለያዩ የሽልማት ገንዘቦች ናቸው፡፡ በዳይመንድ ሊጉ በ12 ከተሞች በሚደረጉ የማጣርያ ውድድሮች  ከ1 እሰከ 8ኛ ደረጃ ላገኙ አትሌቶች በሚበረከተው የሽልማት ገንዘብ መሰረት ለ1ኛ 10ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 6ሺ ዶላር፤ ለ3ኛ 4ሺ ዶላር፤ ለ4ኛ 3ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ 2500 ዶላር፤ ለስድስተኛ 2ሺ ዶላር ፤ ለ7ኛ 1500 ዶላር እንዲሁም ለ8ኛ 1000 ዶላር የሚታሰብ ይሆናል፡፡ በሁለቱ የፍፃሜ ውድድሮች ደግሞ የሽልማት ገንዘቡ ለውጥ የተደረገለት ሲሆን ከ1 እሰከ 8ኛ ደረጃ ላገኙ አትሌቶች በሚበረከተው የሽልማት ገንዘብ መሰረት ለ1ኛ 50ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 20ሺ ዶላር፤ ለ3ኛ 10ሺ ዶላር፤ ለ4ኛ 6ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ 5ሺ ዶላር፤ ለስድስተኛ 4ሺ ዶላር ፤ ለ7ኛ 3ሺ ዶላር እንዲሁም ለ8ኛ 2ሺ ዶላር እንዲከፈል ተደርጓል። በፍፃሜዎቹ የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች ለመሆን የሚበቁት 32 አትሌቶች በነፍስወከፍ ከሚያገኙት የ50ሺ ዶላር ሽልማት በተጨማሪ በአልማዝ ማእድን የተሰራ ልዩ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫ  ይወስዳሉ። 4.9 ኪግ የሚመዝነው የዳይመንድ ሊግ ዋንጫው ተቀማጭነቱ በስዊዘርላንድ ዙሪክ የሆነው፤ ለ250 ዓመታት በዋንጫዎች፤ የክብር ሽልማቶች፤ ሰዓቶች እና ልዩ ልዩ ጌጣጌጦች ስራ የሚታወቀው ክሮኒዮ ሚቲዬሬ የሚሰራ እንደሆነ ታውቋል፡፡ የዳመንድ ሊግ ዋንጫው በ3 የአትሌቲክስ  ገፅታዎች በስታድዬም ፤ በተመልካች ድባብ እና በአትሌት ብቃት መገለጫነት የተቀረፀ ነው፡፡
12 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና 6 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች
የኢትዮጵያ 12 የዳይመንድ ሊግ ድሎች  በ10 አትሌቶች የተመዘገቡ ናቸው፡፡ በ800 ሜትር መሃመድ አማን በ2012 እና በ2013 እኤአ አሸንፏል። በ3ሺ እና 5ሺ ሜትር ወንዶች  በ2010 እና 2011 እኤአ ኢማና መርጋ እንዲሁም በ2013 እኤአ የኔው አላምረው ናቸው። አበባ አረጋዊ ዜግነቷን ሳትለውጥ በፊት በ1500 ሜትር በ2012 እኤአ ላይ አሸናፊ ነበረች፡፡ በሴቶች 5ሺ ሜትር መሰረት ደፋር በ2013 እኤአ ያሸነፈች ሲሆን በ3ሺ ሜትር መሰናክል ደግሞ 2014 እኤአ ላይ ህይወት አያሌው ድል አድርጋለች፡፡ በ2015 ደግሞ ዳይመንድ ሊጉን በ5ሺ ሜትር ለማሸነፍ የበቃችው ገንዘቤ ዲባባ ስትሆን በ2016 እኤአ ደግሞ በ3ሺ እና 5ሺ ሜትር መደብ አልማዝ አያና እና ሃጎስ ገብረህይወት አሸንፈዋል፡፡ በ2017 ኢትዮጵያ የዳመንድ ሊግ ሻምፒዮን አላስመዘገበችም፡፡
በ3ሺ ሜትር የኔው አላምረው በኳታር ዶሃ በ2011 እኤአ ላይ በ7፡27.26
በ5ሺ ሜትር ደጀን ገብረመስቀል በፈረንሳይ ፓሪስ በ2012 እኤአ 12፡46.81
በ10ሺ ሜትር ቀነኒሳ በቀለ በቤልጅዬም ብራሰልስ በ2011 እኤአ 26፡43.16
በሴቶች 1500 ገንዘቤ ዲባባ በፈረንሳይ ሞናኮ በ2015 እኤአ ላይ 3፡50.07 የዓለም ሪከርድ ነው፡፡
በሴቶች 5ሺ ሜትር አልማዝ አያና በሮም ጣሊያን በ2016 እኤአ 14፡14.32
በ10ሺ ሜትር ጥሩነሽ ዲባባ በአሜሪካ ዩጂን 2012 እኤአ ላይ በ30፡24.39
በ8  የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት በሻምፒዮኖችና በክብረወሰኖች የአገራት  ደረጃ
ባለፉት 8 የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት 59 የዳይመንድ ሊግ አሸናፊዎችና 9 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች  ያስመዘገበችው አሜሪካ አንደኛ ደረጃ ይዛለች፡፡ ኬንያ በ37 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና በ8 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች ሁለተኛ ደረጃ ላይ ስትሆን፤ ጃማይካ በ18 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች እና 7 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች ሶስተኛ ፤ ኢትዮጵያ በ2012 እኤአ ላይ አበባ አረጋዊ በ1500 ሜትር ዜግነቷን ወደ ስዊድን ሳትቀይር ያስመዘገበችውን ድል ጨምሮ በ12 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና ስድስት የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች አራተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡

የተቸገሩትን የመርዳትና የመለገስ ልማድ በአለማቀፍ ደረጃ እየቀነሰ ቢመጣም አፍሪካን የመሳሰሉ ድሃ አህጉራት ግን ቸርነታቸውና ደግነታቸው እየጨመረ መምጣቱን ባለፈው ማክሰኞ ይፋ የተደረገ አንድ አለማቀፍ ጥናት አመልክቷል፡፡
በ139 የአለማችን አገራት ላይ የተሰራን ጥናት መሰረት ያደረገው አመታዊው አለማቀፍ የበጎ አድራጎት ልገሳ ሁኔታ አመላካች ሪፖርት እንዳለው፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት የገንዘብ ልገሳ የማድረግ ወይም የማያውቁትን ሰው የመርዳት ልማድ በአለማቀፍ ደረጃ በ2 በመቶ የቀነሰ ሲሆን፣ የበጎ ፈቃደኝነት ተግባር ደግሞ በ1 በመቶ ቀንሷል፡፡
አሜሪካን ጨምሮ የአለማችን ቀዳሚዎቹ 10 ሃብታም አገራት፣ከአምናው ጋር ሲነጻጸር ዘንድሮ በለጋስነት ማሽቆልቆል አሳይተዋል ያለው ሪፖርቱ፤ከአለማችን 20ዎቹ የበለጸጉ አገራት መካከል ከቀዳሚዎቹ 20 ለጋስ አገራት ተርታ መሰለፍ የቻሉት ስድስት ብቻ ናቸው ብሏል፡፡
ላለፉት ሶስት ተከታታይ አመታት የአለማችን እጅግ ቸር እና ለጋስ ህዝቦች መኖሪያ ናት ተብላ በሪፖርቱ በቀዳሚነት የተቀመጠቺው ማይናማር፣ ዘንድሮም የአንደኛነትን ደረጃ ይዛለች ያለው ዘገባው፤ ኢንዶኒዢያ የሁለተኛነት ደረጃን መያዟን አመልክቷል፡፡ በአመቱ በቸርነትና በልግስና ከፍተኛ መሻሻል ያሳየቺው ኬንያ መሆኗን በመጠቆም፣ አምና 12ኛ ደረጃ ላይ የነበረቺው ኬንያ፣ ዘንድሮ ሶስተኛ ደረጃን ላይ መቀመጧንም ገልጧል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ፣ በቸርነት ከአለማችን አገራት የመጨረሻውን ደረጃ የያዘቺው በእርስ በእርስ ጦርነት የፈራረሰቺው የመን መሆኗን አመታዊው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ቻሪቲስ ኤይድ ፋውንዴሽን በተባለው አለማቀፍ ተቋም የተሰራው ጥናቱ፤ የ139 የአለማችን አገራት ዜጎች የሆኑ ከ146 ሺህ በላይ ሰዎችን ቃለ መጠይቅ በማድረግ በተሰበሰበው መረጃ ላይ በመመስረት፣ የአገራቱን ዜጎች የበጎ ምግባር የገንዘብ ልገሳ ተሞክሮ፣ የበጎ ፈቃደኝነት ተሳትፎና የማያውቁትን ሰው የመርዳት ተነሳሽነት በመገምገም ደረጃ እንደሚሰጥም ተነግሯል፡፡

  100 የአመቱ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ አፍሪካዊ የለበትም


       የአለማችንን ዩኒቨርሲቲዎች የጥራት ደረጃ በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው አለማቀፉ የዩኒቨርሲቲዎች ሊግ ሰሞኑንም የአመቱን የአለማችን ምርጥ 100 ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ዘንድሮም እንደ አምናው በአንደኛነት ደረጃ ላይ መቀመጡን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ለ13ኛ ጊዜ ይፋ በተደረገው የአለማችን የምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ የእንግሊዙ ካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛነት ደረጃን ሲይዝ፣ ባለፈው አመት የአለማችን ሁለተኛው ምርጥ የነበረው የአሜሪካው ካሊፎርኒያ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ ዘንድሮ ከአሜሪካው ስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ ጋር የሶስተኛነቱን ደረጃ ተጋርቷል፡፡
8ኛ ደረጃን ከያዘው ኢምፔሪያል ኮሌጅ ኦፍ ለንደን እና 10ኛ ደረጃን ከያዘው የዙሪክ የፌዴራል የቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት በስተቀር፣ ከ3ኛ እስከ 15ኛ ያለውን ደረጃ የያዙት ሁሉም የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ እነሱም ማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ፣ ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ፣ ፕሪንሴተን ዩኒቨርሲቲ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቺካጎ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ፔንሲልቫኒያ፣ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ እና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ካሊፎርኒያ ናቸው ብሏል፡፡  
ከ30ዎቹ የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል ሰባቱ የአውሮፓ ዩኒቨርሲቲዎች ሲሆኑ ሶስቱ ደግሞ የእስያ አገራት ዩኒቨርሲቲዎች ናቸው ያለው ዘገባው፤ እስከ 100 ባለው የአመቱ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ አንድም አፍሪካዊ ዩኒቨርሲቲ አለመካተቱን አክሎ ገልጧል፡፡

  የሩዋንዳ መንግስት በርዕሰ መዲናዋ ኪጋሊ እየተባባሰ የመጣውን የትራፊክ መጨናነቅ ለማስወገድ በማሰብ፣የግለሰቦች የቤት መኪኖች በከተማዋ ጎዳናዎች ላይ እንዳይንቀሳቀሱ የሚከለክል ህግ ተግባራዊ ለማድረግ ማቀዱ ተዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ከቀጣዩ አመት አጋማሽ ጀምሮ ተግባራዊ ሊያደርገው ያሰበው ይህ ህግ፣ በመዲናዋ ኪጋሊ የህዝብ ትራንስፖርት ከሚሰጡና ከተፈቀደላቸው የተቋማት ተሸከርካሪዎች በስተቀር የግል መኪኖች መንቀሳቀስ አይችሉም ሲል ፐልስላይቭ ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
በከተማዋ ለሚታየው ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ የሚገኙት የግል መኪኖች በመሆናቸው የአገሪቱ መንግስት ህጉን ለማውጣት መገደዱንና የህዝብ ትራንስፖርት የሚሰጡ አውቶብሱችን በብዛት ወደ ስራ ለማስገባት ማሰቡን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ህጉ ጸድቆ ተግባራዊ  ከሆነ፣ የቤት መኪና ያላቸው የኪጋሊ ነዋሪዎች፣ ከ2018 አጋማሽ አንስቶ ብስክሌት ወይም የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ አውቶብሶችን ለመጠቀም ወይም በእግራቸው ለመጓዝ ይገደዳሉ ተብሏል፡፡

የብራዚል የቀድሞ ፕሬዚዳንቶች ሉዊስ ሉላ ዳሲልቫ እና ዲልማ ሩሴፍ፣ ግዙፍ የወንጀለኞች ቡድን በማቋቋም ለአመታት ታላላቅ የወንጀል ተግባራትን ሲያከናውኑ ነበር በሚል ባለፈው ማክሰኞ በአገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡
የአገሪቱ አቃቤ ህግ ሁለቱን የአገሪቱ የቀድሞ ፕሬዚዳንቶች እና የፓርቲያቸው አባላት የሆኑ ስድስት ግብረ አበሮቻቸው፣ በስውር ባቋቋሙት የወንጀለኞች ቡድን፤ ሙስናንና የህገወጥ የገንዘብ ዝውውርን የመሳሰሉ የተለያዩ የወንጀል ተግባራትን ሲፈጽሙ እንደነበር በመጥቀስ ክስ መመስረቱን ሮይተርስ ዘግቧል።
በስልጣን ዘመናቸው በሙስና መልክ ከ480 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ አካብተዋል በሚል ክስ የተመሰረተባቸው የቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የሉላ ዳ ሲልቫ እና የአልጋ ወራሻቸው የዲልማ ሩሴፍ ጠበቆች ክሱን መሰረተቢስ ውንጀላ በማለት የተቃወሙት ሲሆን ደንበኞቻቸው ከተባለው የወንጀል ድርጊት ነጻ መሆናቸውን በመጥቀስ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል፡፡
የሰራተኞች ፓርቲ በበኩሉ፤ ክሱ የተመሰረተው ያለምንም ተጨባጭ ማስረጃ ነው፣ ህዝቡ ሌሎች የወንጀል ምርመራ ጉዳዮችን እንዲረሳና ትኩረቱን እንዲቀይር ለማድረግ ታስቦ ሆን ተብሎ የተመሰረተ ክስ ነው ሲል አጣጥሎታል፡፡
አሁንም ድረስ ብዙ ደጋፊዎች ያሏቸውና በመጪው የአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለመወዳደር ያቀዱት የቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሉላ ዳ ሲልቫ፤ ከዚህ ቀደምም የሙስና ክስ እንደተመሰረተባቸው ያስታወሰው ዘገባው፣ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ ለምርጫ እንዳይወዳደሩ ሊያግዳቸው ይችላል ተብሎ እንደሚሰጋም ገልጧል፡፡
በ2002 ወደ ስልጣን የመጡት ሉላ ዳ ሲልቫ፣ለሁለት የስልጣን ዘመን ብራዚልን ካስተዳደሩ በኋላ መንበረ መንግስቱን ለሩሴፍ ማስረከባቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ሩሴፍ በበኩላቸው የአገሪቱን በጀት በህገ ወጥ መንገድ አስተዳድረዋል በሚል በ2016 ከስልጣን መነሳታቸውን አክሎ ገልጧል፡፡

 የአፍሪካ መንግስታት፣ ሽብርተኝነትንና ጽንፈኝነትን ለመዋጋት በማሰብ የሚፈጽሟቸው ድርጊቶችና የሚወስዷቸው እርምጃዎች፣ በተቃራኒው ዜጎችን ወደ ጽንፈኝነት ገፍተው እያስገቡ እንደሆነ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገውና ሶስት አመታትን በፈጀው የጥናት ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ተመድ ይፋ ያደረገው የጥናት ውጤት እንደሚለው፣በአፍሪካ ውስጥ የሚገኙ በመቶዎች የሚቆጠሩ የጽንፈኛ ቡድኖች አባላት፣ የጽንፈኛ ቡድኖችን አስተሳሰብ በመደገፍ አባል ለመሆን የወሰኑት፣ የየአገሮቻቸው መንግስታት በሚወስዷቸው የጸረ ሽብርተኝነትና ጽንፈኝነት እርምጃዎች ተገፋፍተው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የአፍሪካ መንግስታት ቦኮ ሃራምንና አልሻባብን የመሳሰሉ ጽንፈኛና አሸባሪ ቡድኖችን ለመደምሰስ የሚያደርጉት ትግል፣ የአገራቱን ዜጎችና ቤተሰቦቻቸውን ተጎጂ የሚያደርጉባቸው አጋጣሚዎች በርካታ እንደሆኑ የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤ ይህም ዜጎችን ወደ ጽንፈኝነት በመግፋት ያልተፈለገ፣ አሉታዊ ተጽዕኖ እየፈጠረ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡
የጽንፈኛ ቡድኖች አባላት ከነበሩና በጥናቱ ከተካተቱ 500 በላይ አፍሪካውያን መካከል 71 በመቶ የሚሆኑት፣ የአገራቸው መንግስት ጽንፈኝነትን ለመዋጋት በወሰዳቸው እርምጃዎች፣ ቤተሰቦቻቸው ወይም ጓደኞቻቸው መገደላቸው፣ መታሰራቸው አልያም የሌሎች በደሎች ሰለባ መሆናቸው፣ የቡድኖቹ አባል ለመሆን ዋነኛ ምክንያት መሆኑን መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡
በአፍሪካ ባለፉት ስድስት አመታት ብቻ ጽንፈኛ ቡድኖች በፈጸሟቸው የሽብር ጥቃቶችና የጥፋት እርምጃዎች ከ33 ሺህ በላይ የአህጉሪቱ ዜጎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ጽንፈኝነት በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አፍሪካውያንን ለመፈናቀልና ለሰብዓዊ ቀውስ መዳረጉንም አስረድቷል፡፡
አፍሪካውያንን ወደ ጽንፈኝነት እንዲገቡ ይገፋፋሉ ተብለው በጥናቱ ከተለዩት ሌሎች በርካታ ምክንያቶች መካከልም፣ ፍትሃዊ ያልሆነ የሃብት ክፍፍል እንዲሁም የትምህርትና የስራ ዕድል ዕጦት እንደሚገኙበትም ዘ ጋርዲያን በዘገባው ጠቁሟል፡፡

   በዘንድሮ የአዲስ ዓመት ዋዜማ፣ በመዲናዋ የትኞቹ ሆቴሎች፣ ቴአትር ቤቶች፣ የምሽት ክለቦች … የሙዚቃ ድግሶችና  የአውዳመት የመዝናኛ ፕሮግራሞች ተዘጋጅተዋል? ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ እንዲህ ቃኝታቸዋለች፡፡

                 
                   “እንቁጣጣሽ ክላሲክ ኮንሰርት” - በካፒታል ሆቴል

     ባለአምስት ኮከቡ ካፒታል ሆቴል፤ በአዲሱ አመት ዋዜማ ከምሽቱ 12፡00 ጅምሮ “እንቁጣጣሽ ክላሲክ ኮንሰርት” የሚል ስያሜ የተሰጠው የሙዚቃ ድግስ አሰናድቷል፡፡ በዚህ ድግስ ተወዳጆቹ ድምፃውያን ሳሚ ዳን፣ ሚካኤል ለማ ደምሰው፣ ፀደንያ ገ/ማርቆስ፣ የባላገሩ አይዶል አሸናፊ ዳዊት ፅጌ፣ አስገኘሁ አሸኮ (አስጌ ዴንዳሾ) ታዳሚውን በዘፈኖቻቸው የሚያዝናኑ ሲሆን ዲጄ ዊሽና ዲጄ ጆ ዋዜማውን በምርጥ ሙዚቃዎች ያደምቁታል ተብሏል፡፡
በሙዚቃ ድግሱ ላይ ለሚታደሙ ከእራት በፊት ለአንድ ሰው 699 ብር፣ እራትን ጨምሮ 1199 ብር፣ ለጥንዶች ያለ እራት 1199 ብር፣ እራትን ጨምሮ 1999 ብር የሚያስከፍል ሲሆን ዝግጅቱ እስከ ሌሊቱ 8፡00 ድረስ እንደሚዘልቅ የሆቴሉ ማርኬቲንግ ሃላፊ፣ ወ/ሪት ተወዳጅ አሰፋ ለአደስ አድማስ ገልፀዋል፡፡


-----------------

                    ልዩ የእራት ፓርቲ-በኢሊሊ ሆቴል

      ባለ አምስት ኮከቡ ኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ደግሞ በዘመን መለወጫ ዋዜማ ምሽት ልዩ የእራትና የሙዚቃ ድግስ አዘጋጅቷል፡፡ በዚህ ምሽት ኦሮምኛን ጨምሮ የተለያዩ የብሄር ብሄረሰቦች ሙዚቃና ባህላዊ ጭፈራ የሚቀርብ ሲሆን ስታንዳፕ ኮሚዲ፣ የባንድ ሙዚቃና ሌሎችም ዝግጅቶች ተሰናድተዋል ተብሏል፡፡ ጳጉሜ 5 ከምሽቱ 1፡00 ሰዓት ጀምሮ የሆቴሉ በሮች ለታዳሚያን ክፍት ሲሆኑ የመግቢያ ዋጋው እራትን ጨምሮ (ውስኪ መጠጦችን ለሚጠቀሙ) 1500 ብር፣ ከእራት ጋር የወይን መጠጦችን ለሚወስዱ 1 ሺህ ብር መሆኑ ተገልጿል፡፡ ሆቴሉ ከዚህ በተጨማሪም የሞሀ ለስላሳ መጠጦችን፣ ጊዮርጊስ ቢራና አኳ አዲስ ውሃን በነፃ ያቀርባል፡፡ አምራቾቹ ለበዓሉ ስፖንሰር ማድረገቸውን በመግለፅ፡፡  የመዝናኛ ድግሱ እስከ እኩለ ሌሊት እንደሚቀጥል የሆቴሉ የህዝብ ግንኙነትና ማህበራዊ ሚዲያ ሃላፊ አቶ ታሪኩ ዋሲሁን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡  

-----------------

                     ሀሴት አኩስፒክ ባንድ ከአዝማሪዎች ጋር በጎልደን ቱሊፕ ሆቴል

      ቦሌ ኤድናሞል ጀርባ የሚገኘው ባለ አራት ኮከቡ ጎልደን ቱሊፕ ሆቴል በበኩሉ፤ አኩስቲክ ባንድን ከአዝማሪዎች ጋር በማጣመር ዓለም አቀፍና ባህላዊ ሙዚቃን ለማቅረብ በምሽቱ ከሀሴት አኩስቲክ ባንድ ሚኪያስ ፍሬው፣ አይዳ ሰለሞንና ሌሎችም የሚሳተፉ ሲሆን ከአዝማሪዎች ቱፓክ በሚል ቅፅል ስሙ የሚታወቀው አዝማሪ ናርዶስ ከተሰኘች አዝማሪ ጋር ስራውን እንደሚያቀርብ ታውቋል፡፡
በዕለቱ በባህል ዘፈን ላይ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ላበረከቱ ሁለት ዘፋኞች ሆቴሉ እውቅና እንደሚሰጥም ተነግሯል፡፡ በዚህ ምሽት ላይ ለመታደም ለአንድ ሰው እራትን ጨምሮ 699 ብር ሲሆን ለጥንዶች እራትን ጨምሮ 1299 ብር እንደሚያስከፍል የሆቴሉ ማርኬቲንግ ኃላፊ መርሀዊት ፀጋዬ ገልፀዋል፡፡

------------------

                         የጥበብ ድግስ - በብሔራዊ ቴአትር

      አንጋፋው ብሔራዊ ቴአትር አዲሱን አመት ምክንያት በማድረግ ለአንድ ወር የሚዘልቅ የጥበብ ድግስ እንደሚያቀርብ አስታውቋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ እስከ መስከረም 28 ቀን 2010 ዓ.ም በሚዘልቀው የጥበብ ድግስ፤ ከመደበኛው ሙዚቃና ልዩ ልዩ የኪነጥበባት ዝግጅት በተጨማሪ የአረጋዊያን የፋሽን ትርኢት፣ የአርበኞች ልዩ ዝግጅት፣ የአንጋፋው አርቲስት ጥላሁን ገሰሰ የመታሰቢያ ፕሮግራም የ”ሚስ ናሽናል ቴአትር” የቁንጅና ውድድርና ሌሎችም የመዝናኛ ፕሮግራሞች እንደሚቀርቡ ብሔራዊ ቴአትር አስታውቋል፡፡

 ጉዳዩ፡- ሚሊኒየም አዳራሽ ፈርሶ፣ ባለ 5 ኮከብ ኮንቬንሽን ሴንተር


      ክቡርነትዎ፤ ይህችን አነስተኛ ማስታወሻ የጻፍኩት፣ እንደ አንድ የአገር ተቆርቋሪ፣ የአዲስ አበባ ነዋሪነቴ ነው። እንደሚታወቀው፤ የኢትዮጵያ ሚሊኒየምን ለማክበር በታቀደ ጊዜ፣ በወቅቱ  ሰፊ አዳራሽ ባለመኖሩ፣ ሼክ መሐመድ ሁሴን አላሙዲን፣ አዳራሹን ለመስራት ቃል ገቡ፡፡ ይሄን ተከትሎም ለመሥሪያ የሚሆን ቦታ (ካልተሳሳትኩ፣ከሊዝ ነፃ የሆነ) ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ መግቢያ ላይ ተረክበው፣ አዳራሹ በፍጥነት ተሰራ፡፡ ለታለመለት ተግባርም ዋለ፡፡ ሚሊኒየሙ፣ በዘፈንና በጭፈራ በደመቀ ሁኔታ ተከበረ፡፡ ሼክ መሐመድ ሁሴን አላሙዲን፣ ቦታውን ሲረከቡ ግን፣ ይህ በጥድፊያ የተሰራ ኮንቴነር አዳራሽ ፈርሶ፣ በምትኩ በአውሮፓ ስታንዳርድ፣ ዘመናዊ አዳራሽ እንደሚገነቡ ቃል መግባታቸውን  አስታውሳለሁ፡፡
 እነሆ፤ ኢትዮጵያ ሚሊኒየሙን ካከበረች ድፍን አስር አመታት አስቆጥራለች፡፡ የዛሬ 10 ዓመት ለጊዜው ተብሎ የተሰራው ሚሊኒየም አዳራሽ፣አሁንም ባለበት ነው። የተባለው ደረጃውን የጠበቀ አዳራሽ ይሄን ሁሉ ዓመት አልተገነባም፡፡ በእኔ እምነት ሼክ መሀመድ፣ይሄንን አዳራሽ አፍርሰው፣ ባለ አምስት ኮኮብ የሆነ ዓለም አቀፍ ደረጃው የጠበቀ አስደናቂ አዳራሽ ማስገንባት  አያቅታቸውም። ከተማችን አዲስ አበባ፣ የአፍሪካ ዋና ከተማ መሆኑዋ ይታወቃል፡፡ ዓለም አቀፍ ስብሰባዎች ለማካሄድ የምትመረጥ ከተማም እየሆነች መጥታለች። በዚህም የተነሳ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ  አዳራሽ እንደሚያስፈልጋት እሙን ነው፡፡
ክቡር ከንቲባ፡-
ሚሊኒየም አዳራሽ ላለፉት 10 ዓመታት በርካታ የሙዚቃ ድግሶችንና ኤግዚቢሽኖችን እያስከፈለ ሲያስተናግድ ቆይቷል፡፡ ከዚህ አንጻር አሁን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ አዳራሽ ለመስራት የሚያስችል አቅም እንደገነባ መገመት ይቻላል፡፡ እንደ ነጋዴ፣ እንዲህ ከፍተኛ ገቢን የሚያስገባ አዳራሽ ማፍረስ ሊያጓጓ ይችላል፡፡ ነገር ግን ቃል በተገባው መሠረት፣ ስታንዳርዱን የጠበቀ አዳራሽ መገንባት እንዳለበት አምናለሁ፡፡ ይሄንን የማስፈጸም ሃላፊነት ደግሞ የከተማ መስተዳድሩ እንደሆነ ይታወቃል፡፡
ከውጪ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ታላላቅ የሀገር መሪዎችና ጎብኚዎች፣ መጀመሪያ የሚመለከቱት ቦታ ላይ ተገትሮ የሚገኘው ቅርፅ የለሽ ኮንቴነርና ድንኳኖች ፈርሰው ፣አዲስ አበባ የአፍሪካን መዲናነቷን የሚመጥናት፣ ባለ አምስት ኮከብ Convention Center መገንባት አስፈላጊ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ አገር ወዳድ ለሆኑትና ለኢትዮጵያ በርካታ ጥሩ ነገሮች ላበረከቱት ባለሀብት ሼክ መሀመድ፣ ያለኝን አክብሮት ለመግለፅ እወዳለሁ፡፡  ነገር ግን ለጊዜያዊ ችግር ታስቦ የተሰራው 10 ዓመታት ያስቆጠረው ሚሊኒየም አዳራሽ፣ በአዲስ ደረጃውን የጠበቀ አዳራሽ መተካት ያለበት ይመስለኛል። መስተዳደሩም ሃላፊነቱን በአፋጣኝ መወጣት ይገባዋል ብዬ አስባለሁ፡፡  
 በላይ ጨብሲ /ልማታዊ ሀብት/
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.