Administrator

Administrator

በድምፃዊ ዳንኤል ዘውዱ የተሰራው “የዝና” የተሰኘና ነባር ዘፈኖች የተካተቱበት የሙዚቃ አልበም በገበያ ላይ ዋለ፡፡
በ1990ዎቹ መጀመሪያ ላይ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየውን የተስፋዬ ወርቅነህን ተወዳጅ ዜማዎች ሪሚክስ በማድረግና በድጋሚ በመስራት በገበያ ላይ ያዋለው ድምፃዊ ዳንኤል ዘውዱ ለዘፈኖቹ ግጥምና ዜማ ደራሲዎች ተገቢውን ክፍያ መፈፀሙንና የቅጂ መብቱን ጠብቆ መስራቱን ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡
የዘፈኖቹ ግጥሞች የተወሰነ ማሻሻያዎች እንደተደረጉባቸውና በታዋቂ የሙዚቃ አቀናባሪዎች መሰራታቸውንም ድምፃዊው ተናግሯል፡፡  

ላለፉት ሃምሳ አመታት ተስለው የተጠራቀሙ የሰዓሊ ወርቁ ጐሹ የስዕል ስራዎች ለዕይታየ ማቀርቡበት “ላይት” የተሰኘ የስዕል አውደ ርዕይ የፊታችን አርብ ከቀኑ 11 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ሙዚየም አርት ጋለሪ ይከፈታል፡፡
በዚህ አውደ ርዕይ እጅግ በርካታ የስዕል ስራዎች የሚቀርቡ ሲሆን የተለያዩ ጉዳዮችን እንደሚዳስሱም ተገልጿል፡፡
አውደ ርዕዩ እስከ ፌቡራሪ 23 ቀን 2015 ዓ.ም ድረስ ለጐብኚዎች ክፍት ሆኖ እንደሚቆይም አዘጋጁ ጐሹ አርት ጋለሪ ከላከው መግለጫ ለማወቅ ተችሏል፡፡


ቫይረሱ በትንፋሽ መተላለፍ ሊጀምር እንደሚችል ተሰግቷል

በምዕራብ አፍሪካ አገራት ተከስቶ ከ22 ሺህ በላይ ሰዎችን ያጠቃውና ወደ 9 ሺህ የሚደርሱትንም ለህልፈት የዳረገው የኢቦላ ቫይረስ፣ ባህሪውን እየለወጠ እንደሚገኝና ለውጡ ቫይረሱን ከሰው ወደ ሰው በቀላሉ መዛመት እንደሚያስችለው ለማወቅ  ጥናት እየተካሄደ  መሆኑን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የፈረንሳዩን ፓስተር ኢንስቲቲዩት ተመራማሪዎች ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ቫይረሱ የቀድሞ ባህሪውን እየለወጠ እንደሚገኝ የተረጋገጠ ሲሆን ተመራማሪዎቹ የቫይረሱ የባህሪ ለውጥ የከፋ አደጋ የሚያስከትል መሆኑን ለማወቅ  በጊኒ፣ በቫይረሱ በተጠቁ በመቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የደም ናሙና ላይ ምርምር እያደረጉ ይገኛሉ፡፡
የተመራማሪ ቡድኑ አባል የሆኑት ዶክተር አናቫይ ሳኩንታቢ እንዳሉት፤ የኢቦላ ቫይረስ በሚገርም ሁኔታ የተፈጥሮ ባህሪውን እየቀየረ እንደሚገኝ በጥናታቸው አረጋግጠዋል፡፡ ቫይረሶች በጊዜ ሂደት የተፈጥሮ ባህሪያቸውን መቀየራቸው የተለመደ ክስተት ነው ያሉት ዶክተሩ፣ ኢቦላም እንደ ኤች አይቪ ኤድስና ኢንፍሉዌንዛ ቫይረሶች ሁሉ በከፍተኛ ሁኔታ የባህሪ ለውጥ የማካሄድ ተፈጥሯዊ ባህሪ እንዳለው ተናግረዋል፡፡ ይህም ቫይረሱ ከሁኔታዎች ጋር የመላመድ አቅሙን ከፍ እንደሚያደርገውና የበለጠ ሊስፋፋ ይችላል የሚል ስጋት እንደፈጠረ አክለው ገልጸዋል፡፡
ቫይረሱ በርካታ ሰዎችን እያጠቃና የባህሪ ለውጡን እየቀጠለ ከሄደ፣ በትንፋሽ የመተላለፍ ዕድል ሊኖረው ይችላል የሚል ስጋት መኖሩን የተናገሩት ተመራማሪዎቹ፣ ይህም ሆኖ ግን ለጊዜው ቫይረሱ በትንፋሽ እየተላለፈ እንደሚገኝ የሚያረጋግጥ ምንም አይነት ተጨባጭ ማስረጃ አለመኖሩን ገልጸዋል፡፡
በተያያዘ ዜና የአለም ባንክ ፕሬዚደንት ጂም ያንግ ኪም፤ አለማችን በቀጣይ ሊከሰቱ ለሚችሉ ኢቦላን የመሳሰሉ ገዳይ በሽታዎች ይህ ነው የሚባል ዝግጅት አለማድረጓንና ይህም ከፍተኛ ጥፋት ሊያስከትል እንደሚችል አስታወቁ፡፡
መንግስታት፣ የእርዳታ ድርጅቶች፣ አለማቀፍ ተቋማትና ኩባንያዎች ወደፊት ሊከሰቱ የሚችሉ የገዳይ በሽታዎች ወረርሽኞችን ለመከላከልና ለመቆጣጠር እጅ ለእጅ ተያይዘው መስራት ይገባቸዋል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ በምዕራብ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ ጥፋት ካደረሰው የኢቦላ ወረርሽኝ በመማር አለም ከወዲሁ ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅባታል ብለዋል፡፡

የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው አውሮፕላኖችንና መንገደኞችን በማስተናገድ በአለማችን ከሚገኙ አውሮፕላን ማረፊያዎች የመጀመሪያውን ደረጃ መያዙን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2014 ዓ.ም 70 ነጥብ 47 ሚሊዮን መንገደኞችን ያስተናገደው የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ፣ ከዚህ በፊት በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ ቀዳሚነቱን ይዞ የቆየውን የለንደኑን ሄትሮው አውሮፕላን ማረፊያ በመብለጥ በአንደኝነት መቀመጡን ዘገባው አስታውቋል፡፡
የዱባይ አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ ስራ አስኪያጅ ሼህ አህመድ ቢን ሰኢድ አል መክቱም እንደገለጹት፣ በርካታ አለማቀፍ በረራዎችን በማስተናገድ የሚታወቀው አውሮፕላን ማረፊያው የሚያስተናግዳቸውን መንገደኞቹን ቁጥር ባለፉት አምስት አመታት በኣማካይ በሁለት ዲጂት እያሳደገ መጥቷል፡፡
አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው ዱባይን የአለማቀፍ የአየር በረራ ማዕከል የማድረግ ግቡን ወደ ማሳካት እየተቃረበ ነው ያሉት ስራ አስኪያጁ፣ በተያዘው የፈረንጆች አመትም የመንገደኞቹን ብዛት በከፍተኛ ሁኔታ ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡
የአውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው ዋና ስራ አስፈጻሚ ፖል ግሪቭስ በበኩላቸው፣ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያው አዲስ የበረራ ማስተናገጃ በመክፈት፣ አመታዊ የመንገደኞች ማሰተናገድ አቅሙን በያዝነው የፈረንጆች አመት 90 ሚሊዮን ለማድረስ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡
ከዚህ ቀደም በርካታ መንገደኞችን በማስተናገድ በቀዳሚነት ይጠቀስ የነበረው የለንደኑን ሄትሮው አለማቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ጣቢያ በ2014 ያስተናገዳቸው መንገደኞች ቁጥር 68.1 ሚሊዮን እንደነበር ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡

የአፍሪካ ህብረት የአህጉሪቱን ርዕሰ መዲናዎች በመንገድ፣ በባቡርና በአየር በረራ ማስተሳሰር ያስችላል የተባለ ትልቅ ፕሮጀክት ተግባራዊ ለማድረግ ከቻይና መንግስት ጋር የትራንስፖርት የመግባቢያ ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ከቻይና ምክትል ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዚያንግ ሚንግ ጋር የመግባቢያ ስምምነቱን የተፈራረሙት የህብረቱ ሊቀመንበር ንኮሳዛ ድላሚኒ ዙማ፣ ባለፈው ማክሰኞ በአዲስ አበባ የተፈረመውን ስምምነት ህብረቱ እስካሁን ከአጋሮች ጋር ከተፈራረማቸው ስምምነቶች ሁሉ ጉልህ ስፍራ የሚሰጠው ነው ብለውታል፡፡
ዚያንግ ሚንግ በበኩላቸው፤ የመግባቢያ ስምምነቱ የምዕተ አመቱ ትልቅ ሰነድ ነው፣ በአየር በረራ መስክ የተፈረመው ስምምነትም በአፍሪካ ህብረት እና በቻይና መካከል ያለውን ትብብር ወደ አዲስ መስክ ያሰፋ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ከአንደኛው የአፍሪካ ክፍል ወደ ሌላኛው ለመጓዝ የተሻለ አማራጭ ተደርጎ የሚወሰደው የአውሮፓን የበረራ መስመር የተከተለ አካሄድ ነው ያሉት ሚንግ፣ አህጉሪቱ ሰፊ እንደመሆኗ በአውሮፓ የበረራ መስመሮች ላይ ጥገኛ ያልሆነና አገራቱን በቀላሉ የሚያስተሳስር የራሷ የትራንስፖርት አውታር ሊኖራት ይገባል ሲሉ መናገራቸውን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡

አሜሪካ በኩባ የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ እንዳትገባ ያስጠነቀቁት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ራኡል ካስትሮ፤ መሰል ጣልቃ ገብነቶች በሁለቱ አገራት መካከል እንደገና የተጀመረውን ግንኙነት ትርጉም አልባ ያደርጉታል ሲሉ  መናገራቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡ ከ40 አመታት በኋላ ኩባን በመጎብኘት የመጀመሪያው የአሜሪካ ከፍተኛ ባለስልጣን የሆኑት የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ረዳት ጸሃፊ ሮቤርታ ጃኮብሰን ባለፈው ሳምንት አገሪቱን መጎብኘታቸውን ተከትሎ ፕሬዚዳንት ራኡል ካስትሮ የአሜሪካ አካሄድ በኩባ ላይ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ጫና ለመፍጠር ማሰቧን ያመላክታል  ብለዋል፡፡
አሜሪካ ይህንን አካሄዷን የማታስተካክል ከሆነ በሁለቱ አገራት መካከል እንደገና የተጀመረው ዲፕሎማሲያዊ ግንኙነት ትርጉም ያጣል ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ አሜሪካ በውስጥ ጉዳያችን ጣልቃ ለመግባት የምታደርገውን ማንኛውም አይነት ሙከራ አገራቸው በዝምታ እንደማታልፈው አስጠንቅቀዋል፡፡
አሜሪካ በኩባ ውስጣዊ የፖለቲካ ተቃውሞን ለማቀጣጠል እያሴረች ነው ያሉት ራኡል ካስትሮ፣ ይሄም ሆኖ ግን ከዚህ የጣልቃ ገብነት ተግባሯ መታቀብ በምትችልበት ሁኔታ ዙሪያ ከአሜሪካ ጋር ለመምከር ፈቃደኛ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡
ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አገራቸው በኩባ ላይ የጣለችውንና ለአስርት አመታት የዘለቀውን የኢኮኖሚ ማዕቀብ እንድታነሳ ጫና እንዲያሳድሩ ጥሪ ያቀረቡት ራኡል ካስትሮ፣ ኩባንያዎቿ በኩባ የቴሌኮሙኒኬሽን ዘርፍ ላይ እንዲሰማሩ የፈቀደችው አሜሪካ፣ በሌሎች የኢኮኖሚ መስኮች ላይም እንደምትሰራ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል፡፡

   ቴለር ኤንድ ሰንስ የተባለው የእንግሊዝ ኩባንያ፣ የአገሪቱን ኩባንያዎች የመመዝገብ ስልጣን በተሰጠው ካምፓኒስ ሃውስ የተሰኘ የመንግስት ተቋም ላይ፣ ስሜን ሲመዘግብ የአንዲት ፊደል ግድፈት በመፈጸም ለተለያዩ ቀውሶች ዳርጎኛል ሲል በመሰረተው ክስ የ9 ሚሊዮን ፓውንድ ካሳ እንዲከፈለው ፍርድ ቤት እንደበየነ ዘ ኢንዲፔንደንት ዘገበ፡፡
ፍርዱ የተላለፈበት የመንግስት አካል በአገሪቱ በኪሳራ ላይ የሚገኙ ተስፋ ቢስ ኩባንያዎችን በሚመዘግብበት ሰነድ ላይ፣ ከስድስት አመታት በፊት በማንችስተር የሚገኝን ቴለር ኤንድ ሰን የተባለ የከሰረ ኩባንያ ለመመዝገብ ፈልጎ፣ በስህተት የአንዲት ፊደል ግድፈት በመፈጸም ቴለር ኤንድ ሰንስ ብሎ በመመዝገቡና መረጃውን ለህዝብ ይፋ በማድረጉ ነው የኩባንያው ሃላፊዎች ክስ የመሰረቱበት፡፡
ኩባንያው ስሙ ተዛብቶ መመዝገቡንና በኪሳራ ላይ እንደሚገኝ የሚያሳየው መረጃ ለህዝብ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ 250 ሰራተኞቹ ስራ መልቀቃቸውን፣ የብድር አቅራቢ ተቋማትና 3ሺህ ያህል አቅራቢዎችም ከኩባንያው ጋር የነበራቸውን የስራ ግንኙነት ማቋረጣቸውን የኩባንያው ጠበቆች ተናግረዋል፡፡
በምህንድስና ስራ ላይ የተሰማራውና ከ100 አመታት ጀምሮ ወታደራዊ መሳሪያዎችን በማምረት የሚታወቀው  ቴለር ኤንድ ሰንስ ኩባንያ የቀድሞ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ፍሊፕ ዴቪሰን ሰብሪ፣ ከስድስት አመታት በኋላ የፊደል ግድፈቱ መከሰቱን ሰምተው ከሁለት ወራት በፊት ከኩባንያው አመራሮች ጋር ስብሰባ ማድረጋቸውንና ክሱን መመስረታቸውን ተናግረዋል፡፡
በእንግሊዙ ሮያል ኮርት ኦፍ ጀስቲስ ፍርድ ቤት ካሳ እንዲከፍል የተወሰነበት የመንግስት ተቋም በበኩሉ፣ የፊደል ግድፈቱን መፈጸሙን ቢያምንም፣ በኩባንያው ላይ ለፈጠረው ስህተት ይሄን ያህል ገንዘብ በካሳ እንዲከፍል የተጣለበትን ቅጣት ተቃውሟል፡፡

ፕሬዚዳንቱና 160 ባለስልጣናት ጥቁር መኪና ትተው ነጭ ሊሙዚን መጠቀም ጀምረዋል

 በመካከለኛው እስያ የምትገኘው ቱርክሜኒስታን፣ የአገሪቱ ዜጎች ከአሁን በኋላ ጥቁር ቀለም ያላቸው መኪኖችን ወደ ግዛቷ እንዳያስገቡ መከልከሏን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
የቱርክሜኒስታን የጉምሩክ ባለስልጣናት፣ የአገሪቱ ዜጎች ጥቁር ቀለም ያላቸውን መኪኖች ከውጭ አገራት ገዝተው እንዳያስገቡ የሚከለክል ህግ ከሰሞኑ ይፋ ማድረጋቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ባለስልጣናቱ ክልከላውን በምን ምክንያት ተግባራዊ እንዳደረጉት ግልጽ አለማድረጋቸውን አስታውቋል፡፡
ባለስልጣናቱ ከውጭ አገራት መኪና ገዝተው የሚያስገቡ ኩባንያዎችን፣ ከጥቁር መኪኖች ይልቅ ነጭ ቀለም ያላቸውን መኪኖች እንዲያስገቡ እያግባቡ መሆኑን የጠቀሰው ዘገባው፣ ነጭ ቀለም የመልካም ዕድል ተምሳሌት እንደሆነ መግለጻቸውንም ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ጉርባንጉላይ በርዲሞሃመዶቭ፤ ከቅርብ ጊዚያት ወዲህ ጥቁር መኪና መጠቀም ማቆማቸውንና ህዝብ በሚሰበሰብባቸው ስፍራዎችም ነጫጭ ሊሙዚኖችን መጠቀም መጀመራቸውን ያስታወሰው ቢቢሲ፣ እሳቸውን ተከትለውም 160 ያህል የአገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣናት በነጭ ሊሙዚን መዘዋወር እንደጀመሩ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት የቅንጦት መኪና እንዳይገባ የሚከለክል፣ የተለየ ታርጋ ቁጥር መለጠፍና እይታን የሚጋርድ ሽፋን የተለጠፈባቸውን መኪኖች ማሽከርከር የሚያግድ እንዲሁም ሌሎች ከመኪኖች ጋር የተያያዙ ጥብቅ ህጎችን ማውጣቱንና ተግባራዊ በማድረግ ላይ እንደሚገኝም ዘገባው ያመለክታል፡፡

አንድ አፍሪካዊ የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰር ለብዙ ዓመታት በምዕራብ አገራት ትምህርቱን ሲከታተልና ሲያስተምር ቆይቶ ወደ ትውልድ ቀዬው ይመለሳል፡፡
የትውልድ መንደሩ እንደደረሰም አንድ የመንደር ልጅ ሃይቅ ዳር ቆሞ ይመለከታል፡፡ ልጁ ሰዎችን በታንኳ እያሳፈረ የዕለት ጉርሱን የሚቃርም ነው፡፡ ፕሮፌሰሩ ጀልባው ላይ ተሳፍሮ አፍታ እንኳን ሳይቆይ ልጁን በጥያቄ ያጣድፈው ገባ፡፡
ፕሮፌሰር ፡- ፍልስፍና አንብበሃል?
ልጁ ፡- አላነበብኩም
ፕሮፌሰር ፡- ከንቱ ነህ!
ፕሮፌሰር - ሥነ ልቦናስ አንብበሃል?
ልጁ፡- በፍጹም!
ፕሮፌሰር፡- ውዳቂ ነህ!
ፕሮፌሰር ፡- እሺ ታሪክስ?
ልጁ፡- አላነበብኩም
ፕሮፌሰር፡- ለምንም የማትሆን አልባሌ ሰው ነህ!
ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ አደገኛ ማዕበል ተነሳና ጀልባዋን እንደ ጉድ ይንጣት ጀመር፡፡
ፕሮፌሰሩ በታላቅ ፍርሃት እየራደ ልጁ እንዲረዳው ይጮህ ገባ፡፡ ልጁ ፕሮፌሰሩን በትዝብት እያየው፤ “ፕሮፌሰር፤ ዋና አልተማሩም?” ሲል ጠየቀው፡፡ (አሁን ከንቱው ማነው? በሚል ቅላፄ)

Saturday, 31 January 2015 12:48

ዝብርቅርቅ ጥያቄ

….. (እኔ ላንቺ ማሬ)
አበባ ሞልቶልኝ - ዕድሜዬን ቀጥፌ
ቄጤማ እያለ - እኔኑ አንጥፌ
ወፎች ስላልበቁኝ - ጥርሶቼን አርግፌ .....
እኔ ቀልጬልሽ -
ሜዳ ላይ ፈስሼ - ለፍቅሬ ሳበራ
በገዛ መብራቴ -
ልብሽ ሌላ ‘ያየ - ለግብዣ ከጠራ .....”
.
አይጣልብሽ አንቺው - ያ’ይምሮዬ ነገር
አንቺን እያሰብኩኝ - ትዝ የሚለኝ ሀገር
አሁን የኔን ነገር - ምን ይሉታል ማሬ?
ምን ያገናኝሻል - እስቲ አንቺን ካ’ገሬ?
“…..(እኔማ ላ’ገሬ - )
.
“ሀገሬ ተራራሽ” - እያልኩኝ ዘፍኜ
ያ ቀዳዳነቷን - በአፌ ደፍኜ
እየፆምኩ ስጸልይ - ለሀገሩ ጌታ
ሁሌ እያሰርኩኝ - ሁል ጊዜ ስፈታ ..... ”
.
ግድ የለሽም በቃ -
የምር አብጃለሁ - ሙች ለይቶልኛል
እንዴት “ሀገር” ሳስብ -
እግዜር ከነግርማው - ይደቀንብኛል?
.
“ ….(እግዜር ደ’ሞ እኔን - )
ደካማዋ ነፍሴ - ከእቅፉ ርቃ
ነገር ሲጋጭባት - ሺህ ጊዜ ጠይቃ
እሱ እንደሩቅ ሰው - ዝም - ጭጭ - በቃ
ይህን ጊዜ ነፍሴ - በሃሳቧ ደርቃ ....”
.
ገላጋይ እንቅልፌ - አፋፍሶኝ ይነጉዳል
ያ ባካኙ ልቤም - እንቅልፉን ይወዳል!
.
ማሬ
እኔና እግዜሩ - አንቺና ሀገሬ
ጥያቄዎች ነን - በልቤ ‘ስከዛሬ
ስላ’ንዳችን ሳስብ -
ሌላው ብቅ እያለ - እዛው ላይ ነኝ ዞሬ!!