Administrator

Administrator

ከፍተኛ ተሰጥኦ እንዳላት የሚነገርላት የኢትዮጵያ ጃዝ አቀንቃኝ የሺ ደምመላሽ በሚያዝያ ወር አጋማሽ ላይ በኒውዮርክ የሙዚቃ ኮንሰርት እንደምታቀርብ ታዲያስ መፅሄት ዘግቧል፡፡
የጃኖ ባንድና የጂጂን ሥራዎች ያሳተመው የኒውዮርኩ ፕሮዱዩሰር ቢል ላስዌል “ፋኖ” የተሰኘ ዘፈኗን ዳግም አዋህዶ እያቀናበረላት ሲሆን የሺ አዲስ አልበም ከላስዌል ጋር የመስራት ዕቅድ እንዳላት ታውቋል፡፡
ድምፃዊቷ የኒውዮርክ ኮንሰርቷን የምታቀርበው ከ “ቅኔ” ባንድ ጋር ነው ተብሏል። በኢትዮጵያ አይዶል ዳኝነቷ የምትታወቀው የሺ፤ ከያሬድ ሙዚቃ ት/ቤት በፍሉትና በተጓዳኝ በፒያኖ አጨዋወት ተመርቃለች፡፡ አርቲስቷ “ቅኔ” የተሰኘ የመጀመርያ አልበሟን የዛሬ ሁለት ዓመት ለጆሮ ማብቃቷ ይታወሳል፡፡   

የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሕግ ት/ቤት የ50ኛ ዓመት ኢዮቤልዩ በዓሉን አስመልክቶ ብሔራዊ የምስለ ችሎት ውድድር እንደሚያካሂድ ገለፀ፡፡ ከመጋቢት 16-18 የሚካሄደው ውድድር፤ በአለም አቀፍ ወንዞች አጠቃቀም ዙሪያ የተዘጋጀ ሲሆን በአገሪቱ ያሉ የሕግ ት/ቤቶች በሙሉ ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡ የመጨረሻ የዋንጫ ውድድር መጋቢት 18 ከጠዋቱ 2፡30 ሰዓት የሚከናወን ሲሆን በጉዳዩ ላይ ከፍተኛ ምርምር ያደረጉ ምሁር በአገራችን ድንበር ተሻጋሪ ወንዞችን አስመልክቶ ስለሚነሱ የህግ ክርክሮች የማጠቃለያ ንግግር እንደሚያደርጉ የህግ ት/ቤቱ ጠቁሟል፡፡

በደሳለኝ ግርማ (ዲዶስ ሳምናስ) የተፃፉ የአጭር ልብወለድ እና የግጥም ስብስቦችን የያዘ መፅሃፍ በዛሬው ዕለት በሐረር ይመረቃል፡፡
በአንድ በኩል “አድናቂው” በሚል ርዕስ የአጭር ልብወለድ ስብስቦች ያካተተው መፅሃፉ፤ በሌላው በኩል “እግዜርና አፍሪካ” በተሰኘ ርዕስ የግጥም ስብስቦችን ይዟል፡፡ በኤች ዋይ ኢንተርናሽናል የህትመት ሥራ ድርጅት የታተመው መፅሃፉ፤ በ40 ብር ከ50 ለገበያ ቀርቧል፡፡

የፈጠራ ስራዎች ፀረ-ፊውዳል ድርሰቶች አይደሉም የሚል ምሁር ከመካከላችን ይኖራል? ታዲያ ፀረ-ፊውዳል ታጋዩና የመሬት ላራሹ መፈክር አንጋቢው ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ይህን ህዝባዊ ደራሲ ሳያጎላው ያለፈው ሆን ብሎ ይሆን ወይስ ረስቶት?

ይህን ጽሑፍ ያዘጋጀሁት ስለ አንጋፋው ደራሲ አቤ ጉበኛ አንዳንድ ሃሳቦችን ለመሰንዘር ነው። ጽሑፉ ከምርምርም በሉት ከጥናት ሥራ ጋር የሚመደብ አይደለም፡፡ ወፍ በረር ወይም ወፍ ዘለል ምልከታ አይባልም፡፡ በአጭሩ እኔ ስለአቤ የተሰማኝን የገለጽሁበት መላምታዊ ስሜት ነው፡፡
አቤን እኔ በሚገባ ወይም በቅርበት አላውቀውም፡፡ የአቸፈር ሰው መሆኑን፣ ዳንግላ መማሩን የተረዳሁት በቅርቡ ነው፡፡ የእኛ ዘመን ምሁራን “የየት አገር ሰው ነህ?” ተባብለው በይፋ አይጠያየቁም ነበር፡፡ በትምህርት ቤት ዘመኔ “ሰይፈ-ነበልባል” የተባለውን ድርሰቱን ያነበብሁ ይመስለኛል፡፡ በእኔ የጉርምስና ዘመን፣ በእኔ አካባቢ ስሙ እንደ ሌሎች ደራሲዎች ጎልቶ ሲነገር አልሰማሁም፡፡ ወይም የግንኙነት አድማሴ ጠባብ ነው ወይም በጆሮዬ ተኝቼበታለሁ፡፡ አሁን ይህን እያልሁ ያለሁት በዚያ በእኔ ዘመን ላይ ቆሜ መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ አዎ! እንደ ከበደ ሚካኤል፣ እንደ መንግስቱ ለማ፣ እንደ ፀጋዬ ገ/መድህን፣ ሌላው ቢቀር እንደ መንግስቱ ገዳሙ እንኳ በስሙ አይዘመርለትም ነበር፡፡ የፈጠራ ስራው የወረደ ስለሆነ? ፈፅሞ አይመስለኝም፡፡ ሥራዎቹማ! እሳት ጫሪ፣ አነጋጋሪ፣ የአብዮት ማዕበል ጠሪ ነበሩ፡፡ ፀባዩ ከሰው ስለማይገጥም? ይህ በከፊል እውነት ሊሆን ይችላል፡፡ አቤ እከክልኝ-ልከክልህን የማያውቅ በራሱ የሚተማመን የቀለም ሰው ነበር፡፡ ይህን ሁሉ የሆነ ደራሲ ለምን ደመ መራራ ሆነ? መልሱን እኔም አልሰጣችሁም፤ እናንተም እንድትመልሱልኝ አልፈልግም፡፡
በእነዚያ ዘመናት በአቤ ስም ላይ የተጫኑትን ቋጥኞች ከሥር መሰረታቸው ፈልፍሎ ለማወቅ በእርግጥም ጥልቅ ጥናትና ምርምር ይጠይቃል፡፡ እኔ ግን መላምቴን ጎን-ለጎን ባስሔድ ጆሮውን የሚነፍገኝ እንደማይኖር ተስፋ አለኝ፡፡
1. አቤና የአጼው ዘመን
በዚያን ዘመን የነበሩ ደራሲያን፣ አብዛኛዎቹ በቀኝ እጃቸው ብዕር፣ በግራ እጃቸው ሥልጣን የጨበጡ ናቸው፡፡ በዚህም መሰረት የዘመኑ ሹም የሰራው ብቻ ሳይሆን በሩቁ በማንኪያ የነካው ወጥ ሁሉ ይጣፍጥለታል፡፡ ለምን ቢሉ? ወጡ እንዳይጎረና ዙሪያ ከበው የሚያማስሉለት ብዙ ሌቄዎች ከጎኑ ስላሉ … የዚያ ሁሉ ወጥ አማሳይ እጅ ያረፈበት ወጥ ደግሞ በየትኛውም መመዘኛ ሲታይ ላይጣፍጥ አይችልም፡፡
አቤ በዚያን ዘመን የግሽ-አባይ ጎርፍ ከገጠር አምጥቶ ከቀለጠው ከተማ የዶለው ብቸኛ ፍጡር ይመስለኛል፡፡ በቀኝ እጁም የያዘው ብዕር ብቻ ነው፡፡ ብዕሩም በቅኔ ቤት እንጂ በገነተልዑል ግቢ ውስጥ ገብቶ ያልተሟሸ ነው፡፡ ቃላቱም ቱባ-አገራዊ ሽካራ እንጅ ቤተመንግሥታዊ ለስላሳ አይደለም፤ አስተሳሰቡም ደረቅ-ገጠራዊ እንጅ ከተማዊ-ጮሌ አይመስለኝም፡፡ ገፀ-ባህርያቱም አብዛኛዎቹ ከውጭ አገር የኮረጃቸው ሳይሆን ከአካባቢው በተጨባጭ የፈጠራቸው ናቸው። በፖለቲከኞች ቋንቋ ለመናገር፣ አቤ ለዘመኑ ቢሮክራሲ አጎብዳጅ አልነበረም። (አስር ጊዜ አይመስለኝም… ይመስለኛል… የምለው ያለምክንያት አይደለም፡፡ አንድም ከላይ እንደገለጽሁት ጽሑፉ ጥናታዊ አለመሆኑን ለማረጋገጥ ነው፡፡ ሁለትም ለዚህ መረጃ የሚሆን ማጣቀሻ የፈረንጅ ስም ለመጥራት ስላልፈለግሁ ነው፡፡ ሶስትም አገራዊ ሊቃውንትን በመረጃነት እንዳላቀርብ የቀሰምሁት ዘመናዊ የፈረንጅ ትምህርት የሚስበኝ ወደ ነጭ ምሁራን እንጂ ወደ እራሴ ሊቃውንት አለመሆኑን ለማስገንዘብ ጭምር ነው፡፡)
ወደ ተነሳሁበት ነጥብ ልመለስ፡፡ እና! የአቤ ስም በዘመነ አፄ ለምን ገንኖ አልወጣም? ልብ በሉ፤ አቤ በዚያን ዘመን ግራ እጁ ባዶ ቢሆንም ቀኝ እጁ የሚንቦገቦግ የብዕር ሰይፍ ጨብጧል፡፡ ይህ ሰይፈ-ነበልባል የዘውዱን ህዝባዊ የብዕር ሰው ስም በስርአቱ እንዲታፈን መደረጉ ተገቢም ባይሆን የሚጠበቅ ነው፡፡ ያኔ ሥዩመ እግዚአብሔርን መዳፈር ራሱን ፈጣሪን መድፈር ሆኖ ይቆጠራል፡፡ ይህንን የስዩማንን ድፍረት ቅኔ የቆረጠባት ቤተክርስቲያንም ብትሆን በደግ የምትቀበለው አይመስለኝም፡፡ ቀብታ ያነገሰችውን ንጉሥ ከጉያዋ የወጣ ደብተራ፣ በግራ እጁ ስልጣን ያልጨበጠ ብዕረኛ፣ የቁም-ስቅሉን ሲያበላው ቁጭ ብላ አትመለከተውም፡፡ ያኔ! አቤን አውግዢው፤ ወይም የይቅርታ ደብዳቤ አስጽፊው ብትባል አቤን እንዲጽፍ ሳታስገድደው የምትቀር አይመስለኝም፡፡
ንጉሡና በእሳቸው አካባቢ ያሉት መኳንንትና መሳፍንት አቤን የሚመለከቱት እንደ ኮሚኒዝም በጎሪጥ ነው፡፡ በዘመነ አብዮት ቆምጬ፤ “ኢምፔሪያሊዝምን በጎሪጥ ሶሻሊዝምን እንደ በላይ ዘለቀ አያቸዋለሁ” ብሏል አሉ፡፡ ይህ በዘመኑ ቢሮክራሲ የጎሪጥ የሚታይ ሰው፣ ግራ እጁ ባዶ የሆነ፣ ብዕሩ አርፎ የማይተኛ ተንኳሽ፣ በዐይነ-ቁራኛ የሚታይ ሞገደኛ ብዕረኛ፣ እንኳንስ ስም አሞጋሽ፣ አፍ-አካፋች ጓደኛም አይኖረውም፡፡ እንኳንስ በቀኛቸው ብዕር፣ በግራቸው ሥልጣን የጨበጡት ደራሲያን፣ የእነሱ ቅርበት ያላቸውም ንዑስ ደራሲያንም ቢሆኑ አቤን የሚቀርቡ አይመስለኝም፡፡ ከእሱ ጋር መታየት ከእሱ ጋር መፈረጅ ነው፡፡ ከእሱ ጋር መፈረጅ ደግሞ ከእሱ ጋር ግዞት መውረድ ያስከትላል፡፡ በመሆኑም በዘመኑ አቤን የከበቡት ስም አጥፊዎቹ እንጅ ስም አልሚዎቹ አይደሉም ባይ ነኝ፡፡ በቀረው ተመራማሪው ይሙላበት፡፡  
2. አቤና የተማሪው እንቅስቃሴ
እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ተማሪዎች እንቅስቃሴ በአገራችን ብቻ ሳይሆን በመላው ተራማጅ ዓለም ህዝቦች ዘንድ አንቱ የተባለ ማህበር ነበር፡፡ ማህበሩ ጥልቅ ተራማጅ ብቻ ሳይሆን የሶሻሊስት ርዕዮት አለም ተከታይ ጭምር ነበር፡፡ እንቅስቃሴውም በአገር ውስጥ የነበረው ተሰሚነት ቀላል አልነበረም፡፡ የዘውዱን ስርዓት ቦርቡሮ የጣለው ይህ እንቅስቃሴ እንደሆነ ይታመናል፡፡ ምንም እንኳ ዋርዳ ወይም ማማት ወፎች ፈልገው ያገኙትን የሾላ ፍሬ (አብዮት መሆኑ ነው) አንድ ጉራሽ ሳይቀምሱት ዛፉ ላይ ወጥተው ሲንጫጩ፣ የቤተ መንግሥት ጫካ ተንተርሶ፣ እረኛ መስሎ የበግ ለምድ ለብሶ፣ ያደፈጠ ዝንጀሮ የሾላውን ፍሬ ቢቀማቸውም፣ የተማሪው እንቅስቃሴ ለዚያን ጊዜው ለውጥ ያበረከተው አስተዋጽኦ እጅግ ከፍተኛ ነበር፡፡
ይህ እንቅስቃሴ በላይን ንጉሡ አንቀው ከቀበሩት ጉድጓድ አውጥቶ የታጋይ ካባ ያለበሰ ማህበር ነው። ደጃዝማች ታከለን ፈርጣጭ ንጉሥ አጋች ብሎ ያሟካሸ ነው፡፡ ከዘመኑም ደራሲያን መካከል መርጦ የተቡ ብዕርተኞች ብሎ የካበና የሾመ ነው፡፡ ለ“አልወለድም” ደራሲ፣ በግራ እጁ ባዶ ሆኖ ሥርዓቱን ቀድሞ ለተፋለመ ህዝባዊ የብዕር ሰው፣ ማህበሩ ለምን ያኔ! የጎላ ዕውቅና አልሰጠውም? በግሌ ይህ ተራማጁ የተማሪዎች እንቅስቃሴ በመጽሔቶቹ ላይ ስለ አቤ የፃፈውን ነገር አላነበብሁም፡፡
አቤ በሩሲያ ሥነ-ጽሑፍ ውስጥ ሥራው በተራማጅነት ተፈርጆ ሰፊ መድረክ ሲሰጠው፣ ተራማጁ የተማሪው ማህበር ለምን ስለአቤ ምንም ሳይል አለፈ? አቤ የተማሪው ማህበር የቆመለተን ዓለማ ሙሉ-በሙሉ ያሟላ ብዕረኛ ነው፡፡ የዘውድን ሥርዓት በብዕሩ በጽናት ተፋልሟል፡፡ ለዚህም ድፍረቱ ተግዞ ታስሯል፡፡ ከዘመኑ ብዕረኞች መካከል እንደ አቤ የዘውድ ስርዓትን በብዕሩ በግልጽ የሞገተ ደራሲ እንኳን ያኔ፣ አሁንም ያለ አይመስለኝም፡፡ ታዲያ፣ ጉዳዩ ይህ ሆኖ ሳለ፣ በዓላማ የተሳሰረውን ህዝባዊ ደራሲ፣ ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ለምን ስሙን ሊያገነው አልቻለም? እውን “አልወለድም”ን ባያነብ ነው? ሠይፈ ነበልባልን አንብቦ ባይገባው ነው? ቢያንስ “አንድ ለእናቱ” ብቻውን የአቤን ስም ማግነን ይሳነዋል? የዳኛቸው ወርቁን ብቸኛ ልብወለድ “አደፍርስ”ን በየጥናት ክበባት ያስነበበን የተማሪ ማህበር፣ ለምን ከአቤ ስራዎች አንዱን እንድንወያይበት አላደረገም? የአቤስ የፈጠራ ስራዎች ፀረ-ፊውዳል ድርሰቶች አይደሉም የሚል ምሁር ከመካከላችን ይኖራል? ታዲያ ፀረ-ፊውዳል ታጋዩና የመሬት ላራሹ መፈክር አንጋቢው ተራማጁ የተማሪዎች ማህበር ይህን ህዝባዊ ደራሲ ሳያጎላው ያለፈው ሆን ብሎ ይሆን ወይስ ረስቶት? መልሱን ባውቀውም አልነግራችሁም፡፡ እናንተም እንድትነግሩኝ አልፈልግም፡፡ ለምን ብትሉ መላምት እንጅ ጥናትና ምርምር አይደለምና፡፡
3. አቤና ደርግ
“ሶሽያሊስት ነኝ” ያለው የደርግ መንግሥት ሶሽያሊስት አመለካከት ላላቸው የጥበብ ሰዎች ወዳጅ አልነበረም፡፡ ማርክስ ለማለት ማርቆስ የሚሉትን የደርግ አባላት ያስተካከሏቸው ደብተራቸውን ወርውረው፣ ትምህርታቸውን ጥለው ለዘመናት የታገሉለት አብዮት በእርግጥ የፈነዳ መስሏቸው አገር ቤት የገቡት፣ የተማሪውን ማህበር ሲያንቀሳቅሱ የኖሩት እውነተኛ ተራማጆ ናቸው፡፡ እነዚህም ወጣት ተራማጆች በወጉ ሳይደራጁ አገር ቤት ገብተው ደርግ እርስ-በእርስ ያጨፋጨፋቸውና የተረፉትን እራሱ አርዶ አስፋልት ላይ ያሰጣቸው ናቸው፡፡ በአጭሩ ኮትኩተው-አሰልጥነው፣ መግበው ያሳደጉት ውሻ የበላቸው የዋህ ታጋዮች ናቸው፡፡
ወደ አቤ ስመጣ፣ ደርግ በአብዮት ስም የተረከባት አገር እነአቤ ቀደም ብለው በህዝባዊ ብዕራቸው ያደነቋት፣ የዘመሩላት፣ የተጋዙላት ኢትዮጵያ ናት፡፡ እጅግ በርካታ ህዝቦች አንድ-አንድ ጡብ እየጨመሩ በገነቡት ቤት ላይ ደርግ የመጨረሻዋን ጡብ እንኳ ሳያሰቀምጥ የቤቱ ባለቤት እኔ ነኝ አለ፡፡ በእርግጥም ደርግ ምንም አይነት ጡብ በዚህ የቤት ሥራ ላይ አላኖረም፡፡ በአንፃሩ ግን ደርግ በዘውድ ሥርዐት ታማኝነቱ፣ በአጣና ደብዳቢነቱ፣ በግድያ ፈፃሚነቱ፣ ሕንፃ ገንቢ የሆኑ ተማሪዎችን፣ ምሁራንን በአጠቃላይ ምስኪን ገበሬዎችን አሳዶ ይገድል፣ ህዝባዊ የፈጠራ ሰዎችን ያስር፣ ከግዞት እንዳይወጡ በር ዘግቶ ይጠብቅ የነበረ ዋርድያ ነው፡፡ ይህ ዋርድያ የአገሪቱን ስልጣን ከተረከበበት ቀን ጀምሮ በአፉ ሶሻሊዝም እየሰበከ፣ በተግባር ሶሽያሊስት አመለካከት የነበራቸውን የጥበብ ሰዎች ከኢምፔሪያሊዝም ጋር ደምሮ የጎሪጥ ያያቸው ጀመር፡፡ እንደ አቤ ባይበረታባቸውም መንግስቱ ለማና ሌሎችም የደርግ ጥላቻ ዒላማ ነበሩ፡፡
የአቤ ድርሰቶች ለደርግ የተዋጡለት አይመስልም። ለስልጣን ወይም ለገንዘብ የማይንበረከከው አቤ፤ ከጊዜ በኋላ ብዕሩን ወደ ደርግ እንደሚያዞርበት ገብቶታል፡፡ ደርግ የጀመረውን ትውልድ የማጥፋት ዘመቻውን አቤ ዐይቶ እንዳላየ፣ ሰምቶ እንዳልሰማ ሆኖ በፀጋ የሚቀበለው አይሆንም። በዚህም መሰረት አቤን ከአካባቢው አርቆታል፡፡ የ“አልዋለድም” ደራሲ ጭራሮ-እንጨት ሆኖ ያቀጣጠለውን የአብዮት እሳት ቀርቦ እንዳይሞቅ አግዶታል፡፡ ምንም ዐይነት አስተዋጽኦ እንዳላደረገ ሆን ብሎ ወደ ጎን ገፍቶታል። ዛሬም እንደ ትላንቱ አቤ ከሁሉም የተገለለ ብቸኛ ደራሲ ሆኗል፡፡ ዛሬም እንደ ትላንቱ በጃንዳርም ሰላዮች የሚጠበቅ የብዕር ሰው ተብሏል፡፡ ከአቤ ጋር ቆሞ መታየት ሳይቀር ቀይ ሽብርን የሚጋብዝ አስፈሪ ጉዳይ ሆኗል፡፡ የእሱን ብዕር ምርኳዝ አድርገው ሥልጣን ላይ የወጡ ደርጎች ለምን የአቤ ስም እንዲቀበር ፈለጉ? በእርግጥም አቤ በወቅቱ የደርግ ስጋት ነበረ? አዎ! ነበረ፡፡ ምንአልባት በወቅቱ የፈለቁት ሕቡዕ ድርጅቶች መልምለውት ይሆን? ጨርሶ አልተጠጉትም፡፡ አቤ ከእነሱ ሁሉ ባላይ አርቆ የሚያስብ ታጋይ ብዕረኛ ነበር፡፡ አሁን አጠገቤ ቢሆን ኖሮ “ማንም ተልካሻ በተጠራበት ስም ታጋይ፣ ተራማጅ፣ አትበለኝ” ብሎ ይገስፀኝ ነበር፡፡ አቤ ያኔ! ወደ አንዱ ጎራ ጠባ ቢልማ ኑሮውና ቀብሩም የውሻ ባልሆነ ነበር፡፡
የተፋለመለትን ህዝብ አምኖ ለህዝብ መብትና ፍትህ እየጮኸ፣ የተጋዘለት ህዝብ ግን ሳይደርስለት ደሙ-ደመ ከልብ ሆኖ ቀረ፡፡
እና! በፈጣሪ ተሰይሞም ሆነ ጠበንጃ አንግቦ ሥልጣን ላይ የወጣ ሹም ሁሉ ለምን አቤን ጠላው? ለምን አሳደደው? ለምን ሊቀበር የማይችለውን ስሙን ለመቅበር ሞከረ? መልሱን እኔም አልነግራችሁም … እናንተም እንድትመልሱልኝ አልፈልግም፡፡ ጥያቄ?

Saturday, 08 March 2014 13:00

የቀልድ - ጥግ

ትርጓሜ
ጉባዔ፡- ጉባዔ ማለት ታዋቂ ሰዎች ለየብቻቸው ሊሠሩት የማይችሉትን ነገር አንድ ላይ ሆነው በቃ ምንም ሊሠራ አይቻልም ብለው ተስማምተው የሚወስኑበት ስብሰባ ነው፡፡
*   *   *
አንድ ታላቅ ባለሥልጣን ጉባዔን ሲገልፁት፤ “ጉባዔ ማለት የአንድ ሰው መደናበር በተሰብሳቢው ቁጥር ሲባዛ የሚገኝ የስብስብ ብዛት ነው!”
*   *   *
የ25ኛ ዓመት የጋብቻ ቀኑን የሚያከብር አንድ ባል በጣም ተደብሮ ያየው ጓደኛው ሊያፅናናው እየሞከረ ሲያባብለው፤ ባልዬው ብስጭቱን ሲገልፅ እንዲህ አለ፡-
“በ5ኛው የጋብቻ በዓላችን ጊዜ ሚስቴን ልገድላት አስቤ ጠበቃዬን ባማክረው “20 ዓመት ያስፈድርብሃል ተው” ብሎኝ ተውኩ፡፡ እስቲ አስበው ወዳጄ! ይሄኔኮ ከእሥር ቤት ወጥቼ ነበር!”
*    *   *
ዳኛ (ለተከሳሹ)፡- “በአራት አመት ጥብቅ እሥራትና ከአገር እንድትባረር ተፈርዶብሃል፡፡ የምትለው ነገር አለህ?”
ተከሳሹ፡- “ጌታዬ ሁለተኛው ውሳኔ መጀመሪያ ይሁንልኝ!”
*   *   *
ዳኛ፡- “ፍርድ ቤቱ ውሳኔ ከማስተላለፉ በፊት የምታቀርበው ነገር አለ?”
እሥረኛ፡- “ኧረ ምንም የለኝ ጌታዬ! 50 ብር ነበረኝ ጠበቃዬ ወሰደው”
*   *   *
ሴትዮዋ አዋቂ ዘንድ ሄዳ ዕጣ-ፈንታዬን ንገረኝ ትለዋለች፡፡
አዋቂ፡- (መዳፏን እያየላት) አንድ ረዥም ጥቁር ሰውዬ መጥቶ ሲያሳልፍሽ ይታየኛል፡፡”
ሴትዬዋ፡- “ምን ምን ያደርግልኛል ጌታዬ?”
አዋቂ፡- “ስጦታ በስጦታ ያደርግሻል፡፡ ናይት ክለብ ወስዶ አለምሽን ያሳይሻል፡፡ ፍቅር ለዘለዓለም ይኑር! ብለሽ ዋንጫሽን ታነሺለታለሽ”
ሴትዬዋ፡- “ጥቁሩ ሰውዬ ብዙ ገንዘብ አለው ጌታዬ?” አለች ሴትዮዋ ፍንክንክ እያለች፡፡”  
አዋቂ፡- “ምን ነካሽ? ሰውዬውኮ የአንድ ትልቅ ኩባንያ ፕሬዚዳንት ነው፡፡ ከእናት አባቱ 900,000 ብር የሚከራይ አፓርትማ ወርሷል”
ሴትዮዋ፡- “ታድዬ! እንዴት ያለ ፀጋ ፈሰሰልኝ ጌታዬ! አንድ ነገር ብቻ እንድጠይቅዎ ይፍቀዱልኝ ጌታዬ?”
አዋቂ፡- “ጠይቂኝ!”
ሴትዮዋ፡- “ባሌንና ሶስቱን ልጆቼን የት አረጋቸዋለሁ? ምን ይውጣቸዋል?”

ስለማኅበራት የሰጡትን አስተያየት መልሰው እንዲያጤኑት ተጠየቀ
‹‹ማኅበራት በትኩረት ሊመሩና ጉዟቸውም እየተፈተሸ ሊስተካከል ይገባል›› - መንግሥት


የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ‹‹ከዩኒቨርስቲ ተመርቀው ቤተ ክርስቲያንን እንምራ እያሉ ነው፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ ትውፊትና ሥርዓት አላት፤እንዲህ ማለት አይችሉም›› በማለት የሰጡትን አስተያየት መልሰው እንዲያጤኑት በንግግራቸው ቅር የተሰኙ የመንፈሳውያን ማኅበራት አገልጋዮች ጠየቁ፡፡
አገልጋዮቹ ለአዲስ አድማስ እንደተናገሩት፣ አቡነ ማትያስ ይሄን አስተያየት የሰነዘሩት በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ከኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ጋር በመተባበር የካቲት 21 እና 22 ያዘጋጁት ሀገር አቀፍ የስብከተ ወንጌል የምክክር ጉባኤ በተካሔደበት ወቅት ነው፡፡
በምክክር ጉባኤው መዝጊያ ላይ ባደረጉት ንግግር ‹‹በባዮሎጂና ኬምስትሪ እንቀድስ እያሉ ነው፤›› ያሉት አቡነ ማትያስ፤ ‹‹ምን እያልኹ እንደኾን ይገባችኋል›› በማለት ማንን እንደሆነ የማሳየት ያህል የጠቆሙበት አስተያየት ያልተለመደና ጥቂት የማይባሉ የጉባኤውን ተሳታፊዎች ያሳዘነ እንደነበር የጉባኤው  ምንጮች አመልክተዋል፡፡
በምክክር ጉባኤው ላይ ለውይይት በቀረቡ ጽሑፎች፣ እስከ ሰማንያ ሺሕ የሚገመቱ መንፈሳውያን ማኅበራት በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም በአዲስ አበባ እንደሚንቀሳቀሱ የተጠቀሰ ሲሆን  ቤተ ክርስቲያኒቱ ማህበራቱ በሕግና በሥርዐት የሚመሩበት ደንብ አውጥታ እስካልተቆጣጠረቻቸው ድረስ እየተከሠቱና ሊከሠቱ የሚችሉ ችግሮች በቀላሉ እንደማይታዩ ተመልክቷል፡፡
ቅሬታ አቅራቢዎቹ በበኩላቸው፤በማኅበር ሽፋን ለግል ጥቅማቸውና ፍላጎታቸው የሚሯሯጡ፣ የሃይማኖትና የሥነ ምግባር ሕጸጽ የሚታይባቸው ማኅበራት የመኖራቸውን ያህል ጥሩ ሥነ ምግባር ያላቸው፣ ምእመናንን በማትጋት ለበለጠ ሀብተ ጸጋ የሚያበቁ ጠንካራ ማኅበራትም እንዳሉ ገልጸዋል፡፡  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በምክክር መድረክና በቤተ ክህነቱ ጉባኤያት እየታየ ያለው “ማኅበራት አላሰራ አሉን” በሚል በጅምላ የመፈረጅና የመኰነን ዝንባሌ፣ አብዛኞቹ ማኅበራት ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን እያበረከቱ ያለውንና  በቤተ ክህነቱ ቀጥተኛ አቅም ሊሸፈን የማይችለውን ዘርፈ-ብዙ አገልግሎት ያላመዛዘነ ነው ብለዋል -የማህበራት አገልጋዮች፡፡
“በአሁኑ ጊዜ ማኅበራት የአባሎቻቸውንና የበጎ አድራጊ ምእመናንን የገንዘብ፣ የዕውቀትና ሞያዊ አቅም በማስተባበር የገጠር አብያተ ክርስቲያናት፣ ገዳማት፣ አድባራትና የአብነት ት/ቤቶች በተቀናጀ መንገድ እንዲረዱ ያደርጋሉ፤ ለቤተ ክርስቲያንና ለሀገር ዕድገት የሚጠቅሙ ልዩ ልዩ ጥናቶችን ያካሒዳሉ፤ በጠረፍ የሀገሪቱ ክፍል በሚያከናውኑት የስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ ምእመኑ በቋንቋው የሚገለገልበትን ኹኔታ ያመቻቻሉ፤ የቅዱሳት መካናት ተሳላሚዎችን ጉዞ በማስተባበር ሕዝቡ ቅርሱንና ባህሉን አውቆ እንዲጠብቀውና እንዲከባከበው ከማስቻላቸው ባሻገር ለሀገር ውስጥ ቱሪዝም መስፋፋትና መጠናከርም ያላቸው አስተዋፅኦ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡” ሲሉ የማህበራትን ጥቅም አብራርተዋል፡፡
ማኅበራቱ አብዛኞቹን ተግባራት የሚያከናውኑት በየደረጃው ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሓላፊዎች ፈቃድ እያገኙና መመሪያ እየተቀበሉ መኾኑን የሚገልጹት አገልጋዮቹ፣ በግንቦት 2004 ዓ.ም. የማኅበራትን ቁጥር ስለመቆጣጠር ለቅዱስ ሲኖዶስ ቀርቦ በነበረው ጥናት መነሻነት ምልዓተ ጉባኤው ራሱን የቻለና ማኅበራቱን የሚያሠራ ሕግ እንዲዘጋጅ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የሕግ ባለሞያዎች ያሉበት ደንብ አዘጋጅ ኮሚቴ ሠይሞ እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ የማኅበራት አደረጃጀትና የፋይናንስ ቁጥጥር መርሕን ጠብቆ እንደሚወጣ ሲጠበቅ የቆየው ደንብ ከሚገባው በላይ መዘግየቱ ችግሩ ከቤተ ክህነቱ እንጂ ከማኅበራቱ አገልግሎትና ብዛት አለመኾኑን እንደሚያመለክት ይከራከራሉ፡፡
ፓትርያርኩ አድልዎ በሌለው መልኩ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማስተዳደር በዕለተ ሢመታቸው ቃለ መሐላ መፈጸማቸውን የሚናገሩት ቅሬታ አቅራቢዎቹ፣ በምክክር ጉባኤው ላይ በተጠቀሰው አኳኋን የመናገራቸው ግፊት የተለያየ መነሻ ሊኖረው እንደሚችል አስተያየታቸውን ሰንዝረዋል፡፡
የመጀመሪያው መንሥኤ፣ የሙስናንና ብልሹ አሠራርን ችግር ለመቅረፍና ለማድረቅ በቅ/ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ መሠረት ለአዲስ አበባ ሀ/ስብከት የተሠራው የመዋቅር፣የአደረጃጀትና የአሠራር ጥናት ተቃዋሚዎች የጥናቱ ባለቤት ነው በማለት በሚከሡት ማኅበረ ቅዱሳን ላይ በቤተ ክርስቲያኒቱ ከፍተኛ አመራር አማካይነት እንዲፈጠር የሚሹት ጫና ነው፡፡ ኹለተኛው ደግሞ በመንግሥት በኩል፣ ‹‹በኦርቶዶክስ ሃይማኖት ውስጥ አክራሪነትና ጽንፈኝነት የሚታየው ህልውናቸውና ዓላማቸው ሃይማኖታዊና በሃይማኖቱ የበላይ ጠባቂዎች ይኹንታ በተቋቋሙ የወጣት ማኅበራት አደረጃጀቶች ውስጥ በመሸጉ አካላት ነው፤ ስለዚህም ማኅበራት በትኩረት ሊመሩና ጉዟቸውም እየተፈተሸ ሊስተካከሉ  ይገባል፤›› የሚለው ክሥ በመሪዎቹ ላይ ያሳደረው ማኅበራቱን የመቆጣጠር ጫና ነው፡፡
የአክራሪነትንና ጽንፈኝነትን ምንነትና መፍትሔዎችን በሚተነትኑት የመንግሥት ሰነዶች፣ የሃይማኖት ተቋማትን ለአክራሪነትና ጽንፈኝነት ተጋላጭ ያደርጋቸዋል ከሚባሉት ኹኔታዎች ውስጥ÷ የሃይማኖት ተቋማቱ የሰው ኃይል አስተዳደርና የፋይናንስ ሥርዐት ለተከታዩ ሕዝብ ግልጽነትና ተጠያቂነት የሌላቸው መኾናቸው፣ በሙስናና በአስተዳደር በደል ሳቢያ የሚፈጠር ግጭት፣ የሰው ኃይል አስተዳደር በዘመድ አዝማድና በጉቦ እየኾነ የሥራ ብቃት በሌላቸው ሰዎች የሚሠራበት፣ የኦዲት ሪፖርት ቀርቦ የሚተችበትና አስተያየት የሚሰጥበት ሥርዐት አለመዳበሩ፣ ተከታዮችን አክራሪነትን የሚቋቋም በሃይማኖት ዕውቀት የማስታጠቅ ክፍተት ይገኙበታል፡፡
በመንግሥት ትንታኔ መሠረት፣አክራሪነትን የመዋጊያው ቁልፍ መሣሪያ ልማትንና ዕድገትን በማፋጠን የመልካም አስተዳደር ችግርን መቅረፍ፣ሕዝቡን በሃይማኖታዊ ዕውቀት ማስታጠቅ ነው፡፡ የሃይማኖት ተቋማትን ለአክራሪነትና ጽንፈኝነት ተጋላጭ ያደርጓቸዋል የተባሉት የመልካም አስተዳደርና የብልሹ አሠራር ችግሮች÷ ማኅበረ ቅዱሳን በተቃዋሚዎች አላግባብ በሚከሠሥበት የመዋቅር፣ የአደረጃጀትና የአሠራር ለውጥ ጥናት ትግበራ በማፋጠን እንዲኹም ማኅበረ ቅዱሳንን ጨምሮ በርካታ ማኅበራት በመቶ ሺሕ የሚቆጠሩ የገዳማትና የአብነት ት/ቤት ማኅበረሰብን በልማትና ተራድኦ ከመደገፍ ጀምሮ በሚያከናውኑት ሐዋርያዊ ተልእኮ ንቃት ሊወገድ እንደሚችል ቅሬታ አቅራቢዎቹ ያምናሉ፡፡ ከዚኽም አንጻር ፓትርያርኩ ንግግራቸውን መልሰው በማጤን ማኅበራት አገልግሎታቸውን አጠናክረው ለመቀጠል የሚያስችላቸው ኹኔታ እንዲያመቻቹ ጠይቀዋል፡፡

ሬት በትለር (ነገም ሌላ ቀን ነው)

አንድ የፖለቲካ ምርጫ ተሳታፊ፤ ሁሌ የቆሸሸና አልባሌ ልብስ ይለብሱ ነበረ ይባላል፡፡ አደባባይ ከሚገኝ አልባሌ መሸታ ቤት እየገቡ ነበር የሚዝናኑት፡፡ ይሰክራሉ፤ የፖለቲካ ክርክር ያበዛሉ፡፡ ይሟዘዛሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ጨዋና ደግ ነው የሚባለው መራጭ ህብረተሰብ በተመራጩ ቅሬታ ይሰማዋል፡፡ ደጋፊዎቹም በጣም ይቀየሙዋቸዋል፡፡ የህዝቡን ብሶት የሰማ፤ የተመራጩን ተራ መሆን ና ወረዳ መሆን አስመልክቶ ሊያጋልጣቸው የፈለገ አንድ የተቃዋሚ ጋዜጣ አዘጋጅ ሪፖርተሩን ይጠራና፤
“ስማ እኒህን ተመራጭ በተቻለ መጠን ተከታትለህ፤ እንዴት እንደሚደነፉ፣ የሚያገኟቸውን ሰዎች እንዴት እንደሚከራከሩ፣ የሚሳደቧቸውን ስድቦች፣ ከሚያሽኮረምሟቸው ሴቶች ጋር ምን እንደሚባባሉ፤ በደምብ አዳምጠህ ስታበቃ በመጨረሻ ቃለ-መጠይቅ ታደርግላቸዋለህ፡፡ በጥንቃቄ እንድትዘግብ” ይለዋል፡፡
ጋዜጠኛው ተመራጩ ወደሚዝናኑበት መሸታ ቤት ይሄድና እንደተባለው  አግኝቶ ሲከታተላቸው ይቆያል፡፡ በመጨረሻም፤
“ጌታዬ ኢንተርቪው ላደርግዎ ነበር?” ሲል በትህትና ይጠይቃል፡፡
“ስለ ምንድነው … ቃለ …መጠይቅ … እንድሰጥህ የፈለከው?” አሉ ተመራጩ፡፡ ድምፃቸው ክፉኛ ይንተባተባል፡፡
“በአጠቃላይ ስለ ምርጫው”
“መ..ል..ካም” አሉ በተንጀባረረ ቃና፡፡
ጋዜጠኛው ቴፑን ደግኖ ቃለ-መጠይቁን አደረገና አበቃ፡፡ የቀደመውን መልሶ አዳመጠው፡፡ ወደ ፅሁፍ ለወጠው፡፡ በጣም ደነገጠ፡፡ መንተባተብ በመንተባተብ ሆኗል፡፡ ንግግሩ ቁርጥርጥ ያለና ጭራና ቀንዱ የማይያዝ ነው፡፡ በዚያ ላይ የመጨረሻው አረፍተ ነገር አስደንጋጭ ነው፡፡
“ያልመረጥሺኝ ወዮልሽ! ዋጋሽን ታገኛለሽ!” ነበር ያሉትሰ፡፡ ጋዜጠኛው ኢንተርቪውን አርትዖት እንዲያደርግለት ለአለቃው አሳየው፡፡ አለቃውም እንደዚያው ደነገጠና፤
“በል ጠዋት ወደ ቢሮዋቸው ሄደህ የሚያስተካክሉት ነገር ካለ ይዩት በላቸው” አለው፡፡
እንደታዘዘው ጋዜጠኛው ወደተመራጩ ቢሮ ሄዶ “ጌታዬ የሚያስተካክሉት ነገር ካለ አንዴ ያንብቡት?” አላቸው፡፡ ተመራጩ በዞረ-ድምር እየተጨናበሱ፤ አነበቡት፡፡ ውልግድግዱ የወጣ ፅሁፍ ሆኖ አገኙት፡፡  ለጋዜጠኛው መልሰው ወረቀቱን ሲሰጡትሱ፤ “ስማ አንተ ጋዜጠኛ! አንድ ምክር ልስጥህ! ወደፊት በምንም ዓይነት፤ ሰክረህ ቃለ-መጠይቅ አትሥራ! ካሁን በኋላ እንዲህ እያወለጋገድህ ትፅፍና ከጐንህ ታገኛታለህ!! እኛንኮ ነው የምታሳጣን!!”
*   *   *
የዛሬውን የሀገራችንን ሁኔታ ስናየው ልማት እየተካሄደ ያለበት፤ አያሌ ሹም ሽሮች፣ የተካሄዱበት… እንደ ቴሌ፣ መብራት ኃይልና ውሃ ልማት ያሉ ድርጅቶች ተዳክመውና ድክመታቸውን ለማረም ሁነኛ እንቅስቃሴ ሲያሳዩ የማይታዩበት፣ የህዝባችን የዕለት ተዕለት ኢኮኖሚ እየደቀቀ የመጣበት … ህይወት በየአቅጣጫው ዛሬም አሳሳቢ የሆነበት፤ ባለሥልጣን ትላንት ያለውን ዛሬ የሚክድበት፣ አሊያም ትላንት የካደውን ዛሬ የሚያምንበት፤… ወደድንም ጠላንም ግን ዛሬም ኤጭ አይባል የአገር ጉዳይ የምንልበት ነው! ሁላችንንም ያገባናል! ሚዲያዎች ይህንን ሁኔታ በደከመም ሆነ በከረረ መልኩ ሁሌም ሲያሳውቁ ቆይተዋል፡፡ መረጃ ያላገኘ-ህዝብ (uninformed public) በደመ-ነብስ የሚኖር ህዝብ ይሆናልና፡፡ ሀቅን መቀበል የዲሞክራሲ የበኩር ልጅ ነው፡፡
የሀገራችንን ድክመትና ጥንካሬ የሚመለከታቸው አካላት ሊያሳውቁን ይገባል፡፡ ግልፅነት አንዱ መርሀችን ነው ብለናልና የፓርቲና የፓርቲ ግጭት፣ የፓርቲና የመንግሥት አካላት አለመጣጣም፤ የበላይ መኰንንና የበላይ መኰንን አለመግባባት፤ የአለቃና የምንዝር ፍጥጫ፤ የበዝባዥና የተበዝባዥ ህዝብ መካረር፣ የኮንትራባንዲስቶች ሻጥር፣ አሻጥርና የተከላካይ አካላት ግፍጫ፣ ሹም ሽርና የመተካካት ለውጥ፤ የአይነኬ ባለሥልጣናትና የአውቆ ዝሞች ማቀርቀር፤  … ወዘተ ሳይገለፁና ሳይታሰብባቸው ውጥረትን የሚፈጥሩ፣ ችግርን የሚያባብሱ፣ ምሬትና ብሶትን የሚያቁሩ፤ ፍሬ-ጉዳዮች ናቸው፡፡ በጥንቃቄ ሊታሰብባቸው የሚገቡ ናቸው! የእኔን ከተወጣሁ ሌላው እንደ ፍጥርጥሩ ማለት፤ አገርን ከዝብርቅርቅ ቀለምና ከተበጫጨቀ ጨርቅ ተገጣጥማ የተሰፋች ያስመስላታል፡፡
የሀገራችን ሌላው አሳሳቢ ችግር የሥራ-መቀዛቀዝ መንፈስ ነው፡፡ ዛሬም ለምን መባል አለበት፡፡ ጥቅሙ ለማን እንደሆነ የማይታወቅ ሥራ-ቀልባሽ ሂደት ነው፡፡ ያም ሆኖ የብዙ ውስጥ-ውስጡን የበሰሉና ያረሩ ምሬቶች ጥርቅም ይመስላል፡፡ የሰው-ጤፉነትና የበላይነት ስሜት (Superiority complex)ም ሆነ፣ የበታችነትና ራስን ዝቅ-አድርጐ የመመልከት አስተሳሰብ (Infiriority complex) ስሜት፤ የዴሞክራሲያዊ አመለካከት አካላት አይደሉም፡፡ የትምክህተኝነትም (Chauvenism) ሆነ፣ የጠባብ አመለካከት (Narrow Nationalist) ፈርጆች፤ የዲሞክራሲያዊ አመለካከት አካላት አይደሉም፡፡ ያለመቻቻል (Tolerance)፣ ወገንተኛነትና ተዓብዮ የዲሞክራሲያዊ አመለካከት አካላት አይደሉም፡፡ እነዚህን ሁሉ መርምሮ “ዴሞክራሲያዊ ነኝ ወይ?” ብሎ ሁሉም ራሱን በጊዜ መፈተሹ የቀኑ ጥያቄ ነው፡፡
ከቶውኑም የውጪ ባላንጣን (external enemy) አሸንፈናል ብሎ መኩራራት፤ የውስጥ ባላንጣ (internal enemy) መፈልፈያውን ጊዜ (incubation time) እንደሚወልድ በቅጡ ማስተዋል ይገባል፡፡ የማንኛውም ሥርዓት የለውጥ ዕድገት ወይ ዝገት እንደሁኔታው የሚያጐነቁላቸው አያሌ እንግዳ-ብቃዮች ይኖራሉ፡፡ በታሪክ የታየ፣ ያለ፣ የነበረ ነው፡፡
ጉልሁንና ዋናውን ስዕል (the bigger picture) በቅጥ በቅጡ ማየቱ አግባብ የመሆኑን ያህል፤ ጥቃቅኖቹንና አንጓ ካንጓ ማያያዣዎቹን (Political ligaments) አበክሮ ማስተዋል ትልቅ ብልህነት ነው፡፡ የተጀመረው ልማት ይህን ያገናዘበ መሆን አለበት፡፡
Even lies mature ይባላል (ውሸትም እንኳን ይበስላል እንደማለት ነው፡፡) ስልክ ስንተክል፣ ኔትዎርክ ስናሰራጭ፤ መብራት ስንዘረጋ፣ ውሃ ስናስገባ፣ አጥንተንና አቅማችንን ለክተን መሆን አለበት፡፡ የልማት ስትራቴጂ ስንቀይስም አጥንተንና አቅማችንን ለክተን መሆን አለበት፡፡ አለበለዚያ “ቀድሞ ነበር እንጂ መጥኖ መደቆስ
አሁን ምን ያደርጋል ድስት ጥዶ ማልቀስ!” የሚለው ግጥም ይመጣል፡፡ በመሠረቱ ልማትን በጐ በጐውን ማየትና መኩራራት ብቻ ሳይሆን ውስጡ ያለውስ ምሥጥና ግንደ-ቆርቁር ምን ይመስላል? ብሎ፣ ይሆነኝ ብሎ ዐይንን ገልጦ ማየት የአባት ነው፡፡ እሸት እሸቱን እያየን ነቀዙን ካላስተዋልን፣ ምርቱን አይተን የግርዱን ብዛት ካላመዛዘንን፤ ሁሌ “ጉሮ-ወሸባዬ” እያልን፤ ውስጥ-ውስጡን መሽመድመዳችን አይቀሬ ይሆናል፡፡ ነገ ስለ ምርጫ ስናወራም ለህዝቡ ዕውነተኛ ገፅታችንን ማሳየት አለብን፡፡ ከልማቱ ተጠቃሚው፤ ህዝብ መሆን አለበት፤ እንጂ ከላይ ከላዩ ቦጥቧጩ መሆን የለበትም፡፡ ማርጋሬት ሚሼል “ነገም ሌላ ቀን ነው” በሚባለው መፅሀፏ ውስጥ የገለፀችው፣ ሬት በትለር የተባለው በጦርነቱ ጥቅም ያጋብስ የነበረ ነጋዴ፤ “አገር ስትለማ ቀስ በቀስ ሀብታም መሆን ይቻላል፡፡ አገር ስትጠፋ ግን በአንድ አፍታ መበልፀግ ይቻላል” የሚለን ለዚህ ነው!!

ከሳምንት በኋላ በፖላንዷ ከተማ ስፖት በሚካሄደው 11ኛው የዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ሻምፒዮና የሚሳተፈውን የኢትዮጵያ ቡድን ገንዘቤ ዲባባ እና መሃመድ አማን እንደሚመሩት ታወቀ፡፡ በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮናው በወንዶች 800 ሜ፣ 1500 ሜ እና 3000 ሜ እንዲሁም በሴቶች  1500 ሜ እና 3000 ሜ ውድድሮች ኢትዮጵያ 11 አትሌቶችን ታሳትፋለች፡፡ አትሌት ገንዘቤ ዲባባና አትሌት መሃመድ አማን በዓለም በቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ሻምፒዮናው ለወርቅ ሜዳልያ ድሎች ከፍተኛ ግምት የተሰጣቸው ሲሆን አዳዲስ ሪከርዶችን እንደሚያስመዘግቡ ተጠብቀዋል፡፡ ገንዘቤ ዲባባ በዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ሻምፒዮናው ከ2 ዓመት በፊት በ1500 ሜ ያገኘችውን የወርቅ ሜዳልያ ክብር የምታስጠብቅበት ወቅታዊ ብቃት ቢኖራትም በ3ሺ ሜ ተሳታፊ ለመሆን እንደወሰነች ያመለከተው የአለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ዘገባ፤ ሁለት ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ የርቀቱን የዓለም ሪከርድ ለሁለተኛ ጊዜ በመስበር የወርቅ ሜዳልያውን ልትወስድ እንደምትችል ግምት ሰጥቷታል፡፡ ባለፈው 1 ወር ጊዜ ውስጥ በ1500ሜና በ3ሺ ሜትር የቤት ውስጥ ውድድሮች እንዲሁም በ2 ማይል ሩጫ ሶስት የዓለም ሪከርዶችን የጨበጠችው ገንዘቤ በስዊድን ስቶክ ሆልም የ3ሺ ሜትር የዓለም ሪከርድን 8 ደቂቃ ከ16.60 ሰኮንዶች በሆነ ጊዜ ማስመዝገቧ ይታወሳል፡፡ በሌላ በኩል በ800 ሜትር በትራክ እና በቤት ውስጥ የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮናዎች የወቅቱ ኮከብ  አትሌት የሆነው መሃመድ አማን በርቀቱ የወርቅ ሜዳልያ ክብሩን ለማስጠበቅ እንደሚወዳደር ተገልጿል፡፡  መሃመድ አማን በ800 ሜትር ዘንድሮ ያስመዘገበው 1 ደቂቃ ከ44.52 ሴኮንዶች የሆነ ጊዜ የአፍሪካ ሪኮርድ እንደሆነ ያመለከተው የአይኤኤኤፍ ዘገባ ምናልባትም የርቀቱን የዓለም ሪከርድ ሊያስመዘግብ እንደሚችል ጠቁሟል፡፡ የዓለም የቤት ውስጥ የአትሌቲክስ ሻምፒዮናው ከ2 ዓመት በፊት በቱርክ ኢስታንቡል በተካሄደ ጊዜ በ1500 ሜትር የነሐስ ሜዳልያ ያገኘው መኮንን ገብረመድህንና ዘንድሮ በ3ሺ ሜትር  ውጤታማነት አንደኛ ደረጃ የተሰጠው  ሃጎስ ገብረህይወት ለወርቅ ሜዳልያ የተጠበቁ ሌሎቹ የኢትዮጵያ አትሌቶች ናቸው፡፡ በተጨማሪም በወንዶች ምድብ አማን ዎቴ በ1500ሜትር፤ የኔው አላምረው እና ደጀን ገብረመስቀል በ3ሺ ሜትር እንደሚሳተፉ ሲገለጽ፤ በሴቶች ምድብ ደግሞ በ1500 ሜትር አክሱማይትና ኤምባዬ ጉዳይ ፀጋዬ እንዲሁም በ3ሺ ሜትር አልማዝ አያና ህይወት አያሌው ይወዳደራሉ፡፡ በሻምፒዮናው ከ1 እስከ 6 ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች የገንዘብ ሽልማት የሚሰጥ ለ1ኛ 40ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 20ሺ ዶላር እንዲሁም ለ3ኛ 10ሺ ዶላር ይሰጣል፡፡ ለአዲስ የዓለም ክብረወሰን ደግሞ  50ሺ ዶላር ቦነስ እንደሚበረከት ታውቋል፡፡
በዓለም የቤት ውስጥ አትሌቲክስ ሻምፒዮና የተሳትፎ ታሪክ ኢትዮጵያ 19 የወርቅ፤ 5 የብርና 11 የነሐስ በድምሩ 35 ሜዳልያዎችን  በመሰብሰብ ከዓለም አገራት አራተኛ ደረጃ ይዛለች፡፡ በሻምፒዮናው ታሪክ ከምንግዜም ውጤታማ አትሌቶች ተርታ  የሚጠቀሱት  ደግሞ ኃይሌ ገብረስላሴ እና መሰረት ደፋር ናቸው፡፡ ታላቁ አትሌት ሃይሌ ገብረስላሴ በ3ሺ ሜትር 3 የወርቅ ሜዳልያዎችን እንዲሁም በ1500 1 የወርቅ ሜዳልያ ያስመዘገበ ሲሆን በ1997 የ3ሺ ሜትርን ሪከርድ 7 ደቂቃ ከ34.71 ሴኮንዶች እንዲሁም በ1999 እኤአ የ1500ሜ ሪከርድን በ3 ደቂቃ ከ33.77 ሰኮንዶች እንደያዘ ነው፡፡ አትሌት መሰረት ደፋር በበኩሏ በ3ሺ ሜትር 4 የወርቅ፤ 1 የብር እና 1 የነሐስ ሜዳልያዎችን በመሰብሰባቸው ነው፡፡


የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ቅጥር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን  ፈታኝ  እንደሆነበት የተለያዩ ሁኔታዎች ያመለክታሉ፡፡ ፌደሬሽኑ ለሁለት ዓመት በዋና አሰልጣኝነት የመሩትን ሰውነት ቢሻው፤ ምክትላቸውንና የግብ ጠባቂዎችን አሰልጣኝ ካሰናበተ በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ያለ አሰልጣኝ አንድ ወር ሆኖታል፡፡ ለዋና አሰልጣኙ ቅጥር የሚያስፈልጉ ዝርዝር መስፈርቶቹን የቴክኒክና ልማት ኮሚቴ ለፌደሬሽኑ ካሳወቀ በኋላ ክፍት የስራ ቦታ ማስታወቂያው ሰሞኑን ወጥቷል፡፡
ማስታወቂያ
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት አመልካቾችን አወዳድሮ ለመቅጠር ያስቀመጣቸው መስፈርቶች ሃላፊነቱ በከፍተኛ ጫና ውስጥ መውደቁን ያመለክታሉ፡፡ የእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ መስፈርቱን የሚያሟሉ አመልካቾች ማስረጃቸውን ፅህፈት ቤት በግንባር ተገኝተው በማቅረብ መመዝገብ እንደሚችሉ ቢያስታውቅም መቼ የቅጥር ሂደቱ እንደሚፈፀም የሰጠው ፍንጭ የለም፡፡ ፌደሬሽኑ ለቅጥሩ ባወጣው ማስታወቂያ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት  ብቁ የሚሆን ተወዳዳሪ ከታወቀ የትምህርት ተቋም ዲኘሎማ ያገኘና ተመጣጣኝ ወይም ከዛ በላይ የትምህርት ደረጃ ያለው፣ በእግር ኳስ አሰልጣኝነት ከፍተኛ ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው የምስክር ወረቀት ማቅረብ የሚችል፣ በእግር ኳስ የማሰልጠን የCAF “B” ወይም ከዛ በላይ ፈቃድ ላይሰንስ (License) ያለው፣ በብሔራዊ ቡድኖች ወይም በከፍተኛ ሊግ ውድድሮች ደረጃ ከፍተኛ ውጤት ያስመዘገበ፣ ዕድሜው ከ35 በላይ መሆን እንዳለበት አመልክቷል፡፡ የእንግሊዝኛ ቋንቋ መናገር ማንበብና መፃፍ የሚችል፣ በኮምፒዩተር ችሎታ እውቀት ያለው፣ ብሔራዊ ቡድኑን የማስተባበርና የመምራት ችሎታ ያለው፣ከፍተኛ ጫና ባለበት ተቋቁሞ መስራት የሚችልና ፈጣን ውሳኔ የመወሰን ችሎታ ደግሞ ለዋና አሰልጣኝነት የሚወዳደረው አመልካች የሚያስፈልገው ችሎታ እንደሆነም ዘርዝሯል፡፡ ፌደሬሽኑ ለክፍት የስራ ቦታው በጠየቀው የሥራ ልምድ ከ1ዐ ዓመት በላይ በብሔራዊ ቡድኖች ወይም ከፍተኛ ሊጐች ደረጃ በዋና አሰልጣኝነት የሰራ ያሠለጠነ በዓለም አቀፍ ደረጃ የማሰልጠን ልምድ ያለውን እንደሚያበረታታ ገልፆ፤ የቅጥር ሁኔታው     በኮንትራት ሆኖ በሚያስመዘግበው ውጤት እንደ አስፈላጊነቱ ሊራዘም እንደሚችል አስታውቋል፡፡ የሚቀጠረውን አሰልጣኝ ተግባርና ኃላፊነትን በመዘርዘር ካስቀመጣቸው መስፈርቶች መካከል   የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ የስልጠና ዕቅድ መሠረት ያደረገ ዝግጅትና ተግባር የሚያከናውን፤ ብሔራዊ ቡድኑን በማንኛውም ደረጃ ለሚደረጉ ውድድሮች በብቃት የሚያዘጋጅ፤ ብሔራዊ ቡድኑ ለሚያደርጋቸው ጨዋታዎች፣ ውድድሮች በተመለከተ ከጨዋታ በፊት እቅድና ከጨዋታ በኋላ የአፈፃፀም ሪፖርት በወቅቱ በኃላፊነት የሚያቀርብ ፣ የሩብ፣ የግማሽና የዓመት የዝግጅት አፈጻጸም ዕቅድ የሚያቀርብ፤ ከብሔራዊ ቴክኒክና ልማት ኮሚቴ እና ከዲፖርትመንት ጋር ብሔራዊ ቡድኑ ውጤታማ በሚሆንባቸው ሁኔታዎች ላይ ተባብሮ የሚሰራ፤ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ስልጠና እንዲሰጥ በሚጠየቅበት ጊዜ የሚሰጥ፤ ከኘሪሚየር ሊግ እና ከብሔራዊ ሊግ ክለብ አሰልጣኞች ጋር ተቀራርቦ የሚሰራ፤ የሚያሰለጥናቸውን የእያንዳንዱን ብሔራዊ ቡድን ተጫዋቾች የቀድሞ የእግር ኳስ ኘሮፋይል የሚያሰባስብና የሚያደራጅ ፤በአገሪቱ እግር ኳስ ላይ የእግር ኳስ ኘሮፊሽናሊዝም እንዲበረታታ እንዲስፋፋ የሚያደርግና የኢትዮጵያ ወጣት U-17፤ U-20 እና የኦሎምፒክ ቡድንን የሚያግዝ መሆን እንዳለበት አስቀምጧል፡፡
ፈታኞቹ ሁኔታዎች
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ  ቅጥርን በቶሎ እና በስኬታማ ሂደት ለማከናወን የእግር ኳስ ፌደሬሽኑን ፈተና ያከበዱት በርካታ ሁኔታዎች ናቸው፡፡  የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ዋና ብሄራዊ ቡድኑ ያለ ዋና አሰልጣኝ  ወር እንዲያልፍ ከማድረጉ በተያያዘ በፊፋ የወዳጅነት ጨዋታ ፕሮግራም ተገቢውን ዝግጅት እንዳየደርግ ምክንያት ሆኗል፡፡ በሌላ በኩል ፌደሬሽኑ እያዘጋጀ ያለው ስትራቴጂክ እቅድ ገና በይፋ ካለመፅደቁ ጋር በተያያዘ  የአዲስ አሰልጣኝ ቅጥሩን ለማከናወን ግራ መጋባቱም አልቀረም፡፡ አንዳንድ የመረጃ ምንጮች የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ክፍቱን የስራ ቦታ በጊዜያዊ ሹመት ሰጥቶ ደረጃውን የጠበቀ ምርጥ አሰልጣኝ ለመቅጠር በቂ ጊዜ መድቦ ለመስራት ፍላጎት እንዳለውም እያመለከቱ ናቸው፡፡
ለብሄራዊ ቡድኑ ዋና አሰልጣኝነት የሚበቃ ኢትዮጵያዊ አሰልጣኝ ለማግኘት በአገር ውስጥ እየሰሩ ካሉ ባለሙያዎች የጎላ ወቅታዊ ብቃት እና ተገቢ ልምድ ያለው አሰልጣኝ ለማግኘት ያለው እድል መጥበቡም ሌላው ፈተና ነው፡፡ በተያያዘም ለብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት ኢትዮጵያዊ ወይንስ  የውጭ ዜጋ የቱ ይሻላል በሚለው አጀንዳ በስፖርት ቤተሰቡ መካከል የተቀሰቀሰው ውዝግብ የቅጥሩን ሂደት አጓጊ እና አስጨናቂ አድርጎታል፡፡ ፌደሬሽኑ በጊዜያዊነት ለዋና አሰልጣኙ ቅጥር ብቻ ትኩረት መስጠቱም ብሄራዊ ቡድኑ ዓለም አቀፍ ተፎካካሪነት እንዲኖረው ለማስቻል ሙሉ አቅም ያለው ስታፍ ማስፈለጉን አለማስተዋሉም ያሳስባል፡፡ እንደ ጋና አይነት ብሄራዊ ቡድኖች ከዋና አሰልጣኙ ጋር የሚሰሩ ከ13 በላይ የተለያዩ ባለሙያዎች ቀጥረዋል፡፡ በጋና ብሄራዊ ቡድን ከዋና አሰልጣኙ ሌላ አንድ ምክትል አሰልጣኝ፤ ሁለት የግብ ጠባቂ አሰልጣኞች፤ የቴክኒክና የተጨዋቾች ምርጫ የሚመለከታቸው ሃላፊዎች፤ የስነልቦና የምግብ እና የፊዚዮ ቴራፒ አገልገሎት የሚሰጡ ባለሙያዎች፤ የብሄራዊ ቡድኑ ቃል አቀባይ፤ የትጥቅ ሃላፊ፤ ልብስ ሰፊ፤ ከበሮ መቺ ተጠቃሽ የሃላፊነት ስፍራዎች ናቸው፡፡ ይሁንና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌሬሽን ከዋና አሰልጣኙ ቅጥር ባሻገር ለሌሎች የአሰልጣኝ ድጋፍ ሰጪ ባለሙያዎች ቅጥር ስላለው ፍላጎት የሚታወቅ ነገር የለም፡፡ ወይም የታሰበበት አይመስልም፡፡
ሌላው ፈተና የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ በሚያከናውነው ቅጥር የውጭ ዜጋ  ከመረጠ በወቅታዊው የገበያ ሁኔታ  የሚያስፈልገው የደሞዝ ክፍያ ከፍተኛነት ሲሆን ይህንንም ለማሳካት የፋይናንስ ምንጩ ከየት እንደሚገኝ በግልፅ አለመታወቁ ናቸው፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ለዋና አሰልጣኙ ቅጥር የሚከፍለውን ደሞዝ በስምምነት ለማድረግ ይፈልጋል፡፡ በኢትዮጵያ እግር ኳስ በአሰልጣኝነት ከፍተኛው ተካፋይ የነበሩት ሰውነት ቢሻው ይከፈላቸው የነበረው ወርሃዊ ደሞዝ 50 ሺብር በዶላር ሲመነዘር ከ3ሺ ያንሳል ፡፡ ሰውነት ቢሻው ኢትዮጵያዊ በመሆናቸው ክፍያው ተመጣጣኝ ሊሆን በቅቷል፡፡ ይሁንና አንዳንድ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በአሁኑ ጊዜ በአፍሪካ ደረጃ የሚሰሩ ዋና አሰልጣኞች ለየአገሮቹ ዜጋ በወር እስከ 11ሺ ዩሮ የውጭ አገር ዜጋ ከሆኑ ደግሞ እስከ 110ሺ ዩሮ መተመኑ የገበያውን ውድነት ያሳያል፡፡ የግብፅ ብሄራዊቡድን አሰልጣኝ የነበሩት አሜሪካዊ ቦብ ብራድሌይ በወር 35ሺ ዶላር፤ የምዕራብ አፍሪካ ቡድኖችን ያሰለጠኑት ፈረንሳዊ ሄነሪ ሚሸል 50ሺ ዶላር፤  ስዊድናዊ ሰኤሪክሰን አይቬሪኮስትን ሲያሰለጥኑ እስከ 175ሺ ዶላር፤ የካሜሮን አሰልጣኝ የነበሩት ፖል ሌግዌን 80ሺ ዶላር በላይ የሚከፈላቸው ነበሩ፡፡ በቅርብ ጊዜ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሆነው የሰሩት ጋርዚያቶ እስከ10ሺ ዶላር ከዚያም በኋላ የሰሩት ኢፌም ኦኑራ 13ሺ ዶላር ይከፈላቸው እንደነበር ይታወሳል፡፡ ቶም ሴንት ፌይት ደሞዝ ባይከፈላቸውም ሺ ዶላር ተከፍሏቸው ለመስራት ፍላጎት የነበራቸው ሲሆን በናይጄርያ የቴክኒክ አማካሪነት 20ሺ ዶላር በወር ያገኙ ነበር፡፡ሚቾ በሩዋንዳ  ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት ሲሰሩ 16ሺ በኡጋንዳ ደግሞ 25ሺ ዶላር እየታሰበላቸው ነው፡፡ከላይ ከተዘረዘሩት የውጭ ዜጋ አሰልጣኞች መካከል እና አስቀድመው በኢትዮጵያ የሰሩ ባለሙያዎችን ወቅታዊ ዋጋ በመመዘን  ፌደሬሽኑ ለዋና አሰልጣኙ ቅጥር ወርሃዊ ክፍያ እስከ 30ሺ ዶላር ሊያስፈልገው እንደሚችል ይገመታል፡፡
ኢትዮጵያዊ ወይንስ  የውጭ ዜጋ?
ለዋና ብሄራዊ ቡድኑ አሰልጣኝነት ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙ አሰልጣኞች በይፋ ፍላጎቱን የገለፀ እና ያመለከተ ባለሙያ ስለመኖሩ የታወቀ ነገር የለም፡፡ ይሁንና ባለፉት ሁለት ሳምንታት ከተለያዩ የአውሮፓ አህገራት እና በአፍሪካ ውስጥ ታላላቅ ቡድኖችን ያሰለጠኑ 10 ትልልቅ አሰልጣኞች ብሄራዊ ቡድኑን ለመያዝ ያላቸውን ፍላጎት ለፌደሬሽኑ እንዳስታወቁ ከሁለት ሳምንት የእግር ኳስ ፌደሬሽኑን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻህን በማነጋገር በሱፕርስፖርት በተሰራ ዘገባ ተገልጿል፡፡ ይሁንና የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ በሚያከናውነው ቅጥር የውጭ ዜጋ  ከመረጠ በወቅታዊው የገበያ ሁኔታ  የሚያስፈልገው የደሞዝ ክፍያ ከፍተኛነትና ለማሳካት የፋይናንስ ምንጩ ከየት እንደሚገኝ ግልፅ አልሆነም፡፡  ከአገር ውስጥ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን በዋና አሰልጣኝነት ለመረከብ በይፋ ፍላጎታቸውን የገለፁ ባይኖሩም ቀድሞ ዋናውን ብሄራዊ ቡድን ያሰለጠኑት እና የሴቶች ብሄራዊ ቡድንን ያሰለጠኑት ኢንስትራክተር አብርሃም ተክለሃይማኖት ለሃላፊነቱ የታጩበትን ሁኔታ ሳይቀበሉት መቅረታቸው ተነግሯል፡፡ ከዚያ ባሻገር ከኢትዮጵያ ቡና ጋር የፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው እና አሁን በሱዳኑ ክለብ አልሃሊ ሼንዲ  የሚሰራው ውበቱ አባተ ፤ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ክለብ አሰልጣኝ የሆነው ፀጋዬ ኪዳነ ማርያም፤ የመከላከያ ክለብ አሰልጣኝ የሆነው ገብረመድህን ሃይሌ እንዲሁም የቀድሞው የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ አስራት ሃይሌ ለሃላፊነቱ ብቁ ስለመሆናቸው ተባራሪ ወሬዎች  ያመለክታሉ፡፡  ከውጭ ዜጎች መካከል ደግሞ ቤልጅማዊው የቀድሞው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ የነበሩት ቶም ሴንትፌይት ወደ ሃላፊነቱ ለመመለስ ያላቸውን ፍላጎት ለሱፕር ስፖርት ሲገልፁ፤ በአሁኑ ጊዜ የኡጋንዳ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ የሆኑት ሰርቢያዊው ሰርዴጆቪች ሚሉቲን ደግሞ ለአሰልጣኙ ቅጥር የሚጠቅሙ ምክሮችን በመለገስ፤ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ማሰልጠን ታላቅ ክብር መሆኑን  ከ2 ሳምንት በፊት ከስፖርት አድማስ ጋር ባደረጉት ቃለምምልስ መግለፃቸው አይዘነጋም፡፡  በኡጋንዳ ብሄራዊ በድን ዋና አሰልጣኝነት ኮንትራት ያላቸው ሰርዴጆቪች ሚሉቲን ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን የቅጥር  ማመልከቻ ማስገባታቸው አይጠበቅም፡፡ በአንፃሩ ቤልጅማዊው ቶም ሴይንትፌይት የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የቅጥር ማስታወቂያውን ካወጣ በኋላ ለፌደሬሽኑ  ማመልከቻ ሊያስገቡ እንደሚችሉ ይገመታል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን በዋና አሰልጣኝነት ለመምራት ፍላጎታቸውን በተለያየ መንገድ አሳውቀዋል ከተባሉ 10 የውጭ አገር ባለሙያዎች መካከል በይፋ  ለሃላፊነቱ ለኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን የስራ ማመልከቻ ማስገባታቸው እንደማይቀር የተወራላቸው በስፔን ላ ሊጋ በሚወዳደሩ ክለቦች በተጨዋችነት  እና  በአሰልጣኝነትየ25 አመት ከፍተኛ የስራ ልምድ  ያካበቱት የ57 ዓመቱ አንቶኒዮ ሎፔዝ  ናቸው፡፡ እንደሆኑ ሱፕር ስፖርት የገለፀው ከሁለት ሳምንት በፊት ነበር፡፡  ስፔናዊው አንቶኒዮ ሎፔዝ በስፔን ላ ሊጋ ውስጥ አትሌቲኮ ማድሪድ፣ሲቪላ ጨምሮ በተለያዮ ክለቦች በተጨዋችነት ያሳለፉ እና ሴልታ ቪጎን እና ቫሌንሲያን በማሰልጠን ከፍተኛ ልምድ ያካበቱ ፤በደቡብ አፍሪካ ሁለት ክለቦችን ያሰለጠኑና በፊት የቦሊቪያን ብሔራዊ ቡድን ሁለት ጊዜ የኮፓ አሜሪካ ውድድር ተሳታፊ እንዲሆን ያስቻሉ ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ በዓለም 107ኛ፤ በአፍሪካ 17ኛ፤ በምስራቅ አፍሪካ 2ኛ ነው


16 ክለቦች በሚሳተፉበት የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ዛሬ እና ነገ በአንደኛ ዙር ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታዎች በመላው አህጉሪቱ ሲካሄዱ የምስራቅ አፍሪካዎቹ ከተሞች አዲስ አበባ፤ ዳሬሰላም እና ናይሮቢ ትልልቅ ግጥሚያዎችን  ያስተናግዳሉ፡፡ የአምናው የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ሻምፒዮን ደደቢት በነገው እለት የቱኒዚያውን ክለብ ሲኤስ ሴፋክሴዬን በአዲስ አበባ ስታድዬም የሚፋለም ይሆናል፡፡ የቱኒዚያው ክለብ ሲኤስ ሴፋክሴዬን ከሳምንት በፊት በአፍሪካ ክለቦች ሱፕር ካፕ በግብፁ ክለብ አልሃሊ 3ለ2 ተሸንፎ ዋንጫ አምልጦታል፡፡ ባለፈው የውድድር ዘመን የአፍሪካ ኮንፌደሬሽን ካፕ ዋንጫን ያሸነፈው ሲኤስ ሴፋክሲዬን በሱፕር ካፑ የደረሰበትን ሽንፈት በነገው የአዲስ አበባ ጨዋታ ለማካካስ ትኩረት ማድረጉን የቱኒዚያ ጋዜጦች ዘግበዋል፡፡ ደደቢት በአፍሪካ ደረጃ  ብዙም ልምድ ባይኖረውም በደጋፊው ፊት ከባድ ተፎካካሪ ሆኖ በመጫወት በከፍተኛ የግብ ልዩነት ለማሸነፍ ከቻለ የማለፍ እድሉን ሊያሰፋ ይችላል፡፡ በሌሎች የአፍሪካ ሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታዎች በዛሬው እለት ናይሮቢ ላይ የኬንያው ክለብ ጎሮማሃያ ለሁለት ጊዜያት የሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫዎችን ያሸነፈውን የቱኒዚያውን ኤስፔራንስ ሲገጥም፤ ዳሬሰላም ላይ ደግሞ የታንዛኒያው ክለብ ያንግ አፍሪካንስ የአምናው የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ከነበረውና ከሳምንት በፊት የሱፕርካፕ ዋንጫ ያገኘውን የግብፁን ክለብ አልሃሊን ያስተናግዳል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከተመሰረተ ከ70 ዓመታት በላይ ያስቆጠረው የኢትዮጵያ ክለቦች ከፍተኛ ውድድር ፕሪሚዬር ሊግ  ባለፈው የውድድር ዘመን በፉክክር ደረጃው  ከዓለም 107ኛ፤ ከአፍሪካ 17ኛ እንዲሁም ከምስራቅ አፍሪካ 2ኛ ማግኘቱን የእግር ኳስ ስታትስቲክስ እና ታሪክ ዓለም አቀፍ ፌደሬሽን (IFFHS) አመለከተ፡፡ ተቀማጭነቱን በስዊዘርላንዷ ከተማ ሉዛን ውስጥ ያደረገው የእግር ኳስ ስታትስቲክስ እና ታሪክ ዓለም አቀፍ ፌደሬሽን (IFFHS)  ለዓለም የእግር ኳስ ሊጎች ደረጃ የሚያወጣው በአገር ውስጥ የሊግ እና የጥሎ ማለፍ ውድድሮች በመመዘን፤ በአህጉራዊ እና በዓለም አቀፍ ደረጃ የየአገሩ ክለቦች ያላቸውን ፉክክር  ደረጃ እና ውጤት በማስላት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ከዓለም የክለብ ውድድሮች 107ኛ ደረጃን  ያገኘው 157 ነጥብ በማስመዝገብ ነው፡፡ በምስራቅ አፍሪካ በክለቦቿ የሊግ ውድድር አንደኛ የሆነችው 230 ነጥብ በማስመዝገብ ከዓለም 91ኛ ደረጃ የወሰደችው ሱዳን ስትሆን፤ የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ከያዘው ሁለተኛ ደረጃ በመቀጠል፤ የኬንያ ፕሪሚዬር ሊግ  በ123 ነጥብ ከዓለም 114ኛ፤ የታንዛኒያ  ፕሪሚዬር ሊግ በ114.5 ነጥብ ከዓለም 118ኛ፤ የብሩንዲ ፕሪሚዬር ሊግ በ114 ነጥብ ከዓለም 119ኛ፤ የኡጋንዳ ፕሪሚዬር ሊግ በ114 ነጥብ ከዓለም 120ኛ እንዲሁም የሩዋንዳ ፕሪሚዬር ሊግ በ108 ነጥብ ከዓለም 125ኛ ደረጃ በማግኘት ተከታታይ ደረጃ አላቸው፡፡ የእግር ኳስ ስታትስቲክስ እና ታሪክ ዓለም አቀፍ ፌደሬሽን (IFFHS)  የዓለም አንደኛ ምርጥ ሊግ ብሎ የሰየመው 1155 ነጥብ ያስመዘገበውን የስፔኑ ፕሪሚዬራ ሊጋ ሲሆን፤ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በ1128 ነጥብ፤ የጀርመን ቦንደስ ሊጋ በ1058 ነጥብ፤ የጣሊያን ሴሪ ኤ በ927 ነጥብ፤ የብራዚል ሴሪኤ በ896 ነጥብ፤ የአርጀንቲና ፕሪሚዬራ ዲቪዥን በ868 ነጥብ፤ የፈረንሳይ ሊግ 1 በ796 ነጥብ፤ የሩስያ ፕሪሚዬር ሊግ በ739.5 ነጥብ፤ የኮሎምቢያ ፕሪሚዬር ሊግ በ724.5 ነጥብ እንዲሁም የሮማንያ ፕሪሚዬር ሊግ በ722.5 ነጥብ ከ2 እስከ 10 ያለውን ደረጃ አግኝተዋል፡፡ በአፍሪካ በምርጥ የፉክክር ደረጃው አንደኛ የተባለው 469.5 ነጥብ በማስመዝገብ በዓለም 31ኛ ደረጃ የወሰደው የቱኒዚያ ሊግ ነው፡፡  ግብፅ በ361.5 ነጥብ ከዓለም 46ኛ፤ ሞሮኮ በ361 ነጥብ ከዓለም 47ኛ፤ ናይጄርያ በ332.5 ነጥብ ከዓለም 53ኛ፤ ማሊ በ322 ነጥብ ነጥብ ከዓለም 56ኛ፤ ደቡብ አፍሪካ በ316.5 በዓለም 61ኛ፤ አልጄርያ በ315.5 ነጥብ ከዓለም 62ኛ፤ አንጎላ በ314.5 ነጥብ ከዓለም 64ኛ እንዲሁም ካሜሮን በ295 ነጥብ ከዓለም 70ኛ በመመዝገብ በአፍሪካ ምርጥ ሊጎች የደረጃ ሰንጠረዥ ከ2 እስከ 10 ተከታትለው ተቀምጠዋል፡፡ ጋና፤ ኮትዲቯር፤ ኮንጎ ዲ ሪፖብሊክ፤ ሱዳን፤ ዛምቢያ፤ ዚምባቡዌ፤ ኮንጎ ኪንሻሳ፤ ኢትዮጵያ፤ በርኪናፋሶ፤ ቦትስዋና እና ኬንያ ከ11 እስከ 20 ደረጃ ያገኙ የአፍሪካ ሊጎች ሆነዋል፡፡