Administrator

Administrator

ሜጀር ጀነራል አደም መሀመድ የአየር ሀይል አዛዥ ሆነው መሾማቸውንና የአዛዥ ጄነራሎች ላይም የምደባ ለውጥ መደረጉን ምንጮቻችን አመለከቱ፡፡ በአየር ሀይል አዛዥ በነበሩት ሜጀር ጀነራል ሞላ ሀይለማርያም ምትክ የተሾሙት ሜጀር ጀነራል አደም የአየር ሀይል ፓይለት የነበሩና በሱዳን አቢዬ ግዛት የሠላም አስከባሪ ሀይል ምክትል አዛዥነት ያገለገሉ እንዲሁም የመከላከያ ዘመቻ መምሪያ ኃላፊ ነበሩ፡፡
በሌሎች የመከላከያ የስራ ምድብ ቦታዎች ላይ የአዛዦች የምደባ ለውጥ መደረጉን የተናገሩት ምንጮች፣ አዲስ የሀላፊነት ምደባ ከተሠጣቸው ውስጥ ሌተናል ጀነራል ሠአረ መኮንን፣ ሌተናል ጀነራል አበባው፣ ሜጀር ጀነራል ዮሀንስ ወልደጊዮርጊስ፣ ሜጀር ጀነራል ገብራት አየለ እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡
ባለፈው አመት እና ዘንድሮ ከ60 በላይ ለሚሆኑ መኮንኖች የጀኔራልነት ሹመትና እድገት መሰጠቱ ይታወሳል፡፡

በአዲስ አበባ በሚገኘው የግሪክ ኮሙኒቲ ስኩል የሚመሩ ህፃናትና ታዳጊዎች ከአንድ ወንዝ የተቀዱ አይደሉም፡፡
ከ60 በላይ የተለያየ ዜግነት ያላቸው በመቶዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎችን የሚያስተናግድ ት/ቤት ነው። የ60 አገራት ተወላጅ የሆኑ ተማሪዎች ስላሉበትም ነው፤ የተባበሩት መንግስታት ቀን በየአመቱ በትምርት ቤቱ የሚከበረው፡፡ ትናንት አርብ ረፋዱ ላይ በተከናወነው ክብረ በዓል፣ የባንዲራዎች ሰልፍ የተካሄደ ሲሆን፤ የግሪክ፣ የምዕራብ አፍሪካ፣ የህንድ እና የኢትዮጵያ የዳንስ ወይም የውዝዋዜ ትርዒት በተማሪዎች ቀርቧል፡፡
በክብረ በዓሉ ላይ የተባበሩት መንግስታት ተወካዮችና የመንግስት ባለስልጣናት በእንግድነት መገኘታቸውን አስተባባሪው ጆሴፍ ፍራንሲስ ገልፀዋል፡፡

ሪም የህፃናት ሞግዚት ማሰልጠኛ ተቋም፣ ለሶስት ወራት ያሰለጠናቸውን 200 ተማሪዎች ዛሬ በሆሊሲቲ ሲኒማ አዳራሽ ያስመርቃል፡፡
ከአዲስ አበባ የቴክኒክና ሙያ ኤጀንሲ እውቅና ያገኘው “ሪም”፣ እውቅና ያለው በየሶስት ወሩ 200 ያህል ሞግዚቶችን ከማሰልጠንም በተጨማሪ ስራ እንደሚያስቀጥር ተገልጿል፡፡
ስልጠናው የህፃናት አስተዳደግን፣ የህፃናት የተመጣጠነ ምግብ ዝግጅትን፣ የህፃናት ጨዋታ አመራረጥ ፣ የመጀመሪያ ደረጃ የህክምና እርዳታ አሰጣጥን ያካትታል ተብሏል፡፡

አዲሱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ
አቶ ጁነዲን ባሻህ የኢትዮጵያን እግር ኳስ ፌዴሬሽንን ለሚቀጥሉት አራት አመታት በፕሬዝዳንትነት እንዲመሩ የተመረጡት ዋልያዎቹ የዓለም ዋንጫ ጥሎ ማለፍ የመጀመርያ ጨዋታቸውን በአዲስ አበባ ከማድረጋቸው ሶስት ቀናት ቀደም ብሎ በተካሄደው ጠቅላላ ጉባዔ ነበር፡፡ የድሬደዋ ከተማ መስተዳድርን በመወከል በምርጫው ተወዳድረው ድምፅ ከሰጡት 106 የጠቅላላ ጉባዔ አባላት የ55ቱን ድምፅ በማግኘት አዲሱ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ሆነዋል፡፡ አቶ ጁነዲን ላለፉት 20 ዓመታት ከስፖርቱ ጋር ትስስር ነበራቸው፡፡ በተለይም የሐረር ቢራ ክለብ ዋና ስራ አስኪያጅ ሆነው በሰሩበት ወቅት ክለቡን ለፕሪሚየር ሊግ አብቅተውታል፡፡ ስለዓላማቸው በኢትዮጵያ እግር ኳስ አስተዳደር ግልፅነትና ተጠያቂነት ለማስፈን እሰራለሁ ብለዋል፡፡

በመላው አገሪቱ እግር ኳስን በተሻለ ደረጃ ለማስፋፋት ተስፋ እንደሚያደርጉ በመግለፅ፤ ስፖርቱን በተረጋጋ የለውጥ ሂደትና በዘመናዊ መዋቅር ለመምራት እንደሚፈልጉና በወጣት ፕሮጀክቶች ትኩረት ሰጥተው እንደሚሰሩም ቃል ገብተዋል፡፡ በንግድና ኢንቨስትመንት ስራዎች ከፍተኛልምድ ያላቸው አቶ ጁነዲን ባሻህ እግር ኳስ ከዝንባሌ ባሻገር ትልቅ ንግድ እንደሚሆን በተግባር የማሳየት ፍላጎት እንዳላቸው ያስገነዝባሉ፡፡ ክለቦች የገቢ ምንጮቻቸውን በማስፋት ሊለወጡ በሚችሉበት የእድገት አቅጣጫ ላይ በጋራ ለመስራት ዝግጁ ናቸው፡፡ አቶ ጁነዲን ባሻህ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንት ሆነው በተሾሙበት እለት ከዚህ በታች የቀረበውን አጭር ቃለምምልስ ከስፖርት አድማስ ጋር አድርገው ነበር፡፡
በሃላፊነት ሳምንት እንኳን ሳይሞላዎት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወደ ዓለም ዋንጫ ለማለፍ ወሳኝ የጥሎ ማለፍ ትንቅንቁን በሜዳው ይጀምራል፡፡ ሁኔታውን እንዴት ይመለከቱታል?
በአንድ በኩል የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ለአለም ዋንጫ ባያልፍ ምን ይመጣ ይሆን የሚለው ያስጨንቀኛል። እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ ውጤት እንዲመጣ ከመጓጓት ነው። አሁን ደግሞ ሃላፊነት ላይ እንደተቀመጠ ሰው በዚህ ሽግግር የተጨናነቁ ነገሮች እንዳይመጡ ፍላጐቴ ነው፡፡ ቢቻል ከቀድሞው አመራር ጋር በቦታው ተገኝተን ቡድናችንን በጋራ ብናይ፣ በሰከነ ሁኔታ ተጨዋቾቻችን እንዲጫወቱ ፤ ተመልካቾችም ድጋፍ እንዲሰጡ አስባለሁ፡፡ በአጠቃላይ መልካም ነገር እመኛለሁ። ዋሊያዎቹ መልካም ነገር እያስመዘገቡ ነው የመጡት፡፡ አሁንም የምንጠበቀው ይህን ነው፡፡ የአመራር መለዋወጥ ከውጤቱ ጋር ብዙም የሚነካካ ነገር የለውም፡፡
ዋልያዎቹ ለዓለም ዋንጫ ቢያልፉ ለኢትዮጵያ ዘርፈ ብዙ ጥቅሞችን ያመጣል፡፡ እርስዎ ምን ይጠብቃሉ?
በኢትዮጵያ የስፖርት ታሪክ ተመልካች ስታድዬም እየገባ በእግር ኳስ ውጤት እያዘነ የወጣበት ዓመታት ብዙ ናቸው፡፡ ለዚህ ተመልካችና ለዚህ ህዝብ ብሄራዊ ቡድኑ ለዓለም ዋንጫ ቢያልፍ መቼም ለሁላችን የሚፈጠረው ደስታ መጠን ያለው አይመስለኝም። እንግዲህ ይህን የሚፈጽሙት ሜዳ የሚገቡት ተጫዋቾች እና የብሄራዊ ቡድኑ አጠቃላይ አባላት ናቸው፡፡ አደራውን ለተጨዋቾችና ለአሠልጣኝ ነው የምሰጠው፡፡ በአጠቃላይ ለዓለም ዋንጫ ማለፍ በአፍሪካ እና ዓለም ደረጃ ጥሩ ገጽታ ይፈጥርልናል ብዬ ነው የማስበው፡፡
ድሮ ኳስ ስንት ቁጥር ለብሰው ነበር የሚጫወቱት?
በተማሪነቴ ስምንት ቁጥር ለብሼ ነበር የምጫወተው፡፡
ከውጭ ኳስ የማን ጨዋታ ደስ ይልዎታል?
የእንግሊዝ እና የስፔን ክለቦችን በብዛት እከታተላለሁ፡፡
የሚያደንቁት ተጫዋችስ?
በፊት ለአርሰናል ይጫወት የነበረው ሄነሪ በጣም ደስ ይለኝ ነበር፡፡ አሁን ደግሞ የሮናልዶና የሜሲ አጨዋወት በጣም ይስበኛል፡፡
ዋልያ የሚለው ቅፅል ስም ተስማምትዎታል?
በአገራችን ያለ ብርቅዬ እንስሳ ስለሆነ አዎ ለአለም ላይ የቱሪዝም ሃብታችንን ማስተዋወቅ ነው፡፡
የድሬድዋ ሰው ኳስን የሚወደው በምን የተነሳ ነው?
ድሬዳዋ ሜዳው ለጥ ያለ ነው፡፡ አሸዋ ነው፡፡ ብትወድቅም ብትንከባለልም፡፡ የሚወስደን ጐርፉ ብቻ አይደለም፡፡ አሸዋውም ላይ ኳሱም አለ፡፡ ህዝቡ በተፈጥሮው ለፊልም፣ ለቲያትር በአጠቃላይ ለጥበብ የተሰጠ ነው፡፡ ባህሉ ሰውን የሚያቀራረብ ነው፡፡ ድሬደዋ ለጅቡቲ ካላት ቅርበት በብዙ መልኩ የአለምአቀፍ ዕሳቤ እና ስልጣኔ አላት፡፡ ስፖርት ደግሞ ስልጣኔ ነው፡፡ በስፖርቱ መስክ የሚመዘገብ እድገት እና ለውጥ የስልጣኔ መገለጫም ይሆናል፡፡
ወደ ስፖርት ከገቡ ከ20 ዓመታት በላይ አስቆጥረዋል። በእነዚህ ጊዜያት ብዙ አመራሮች በፌደሬሽኑ አስተዳደር ተቀያይረዋል፡፡ እርስዎ የፌደሬሽን አመራር እሆናለሁ ብለው አስበውት ያውቃሉ?
ስፖርት ያረካኝ ነበር፡፡ ስፖርትን ኳስ በመምታት አይደለም የማስበው ከዛ በላይ ነው፡፡ ክለብ ስናቋቁምም ወጣቱ የሚያተኩርበት ነገር እንዲያገኝ ከሚል ነው፡፡ አንዳንዴ ያሰብክበት ብቻ አይደለም የምትውለው ፈጣሪ የትም አውሎ ያስገባኝ የምትልበት ጊዜ አለ፡፡

 

              ፈረንሳይ ከሌላው ሀገር የተለየ ቅርስ ወይም የተፈጥሮ መስሕብ የላትም፡፡ ነገር ግን ከሕዝብ ቁጥሯ በሚሊዮኖች የላቀ ቱሪስት በየዓመቱ ይጎበኛታል፡፡ ጎረቤቷ ጣሊያን ከፈረንሳይ በቁጥር የበለጡ ዓለምአቀፍ ቅርሶች ብታስመዘግብም እንደ ፈረንሳይ አልጎረፈላትም፡፡
ኢትዮጵያም ዓለም አቀፍ ቅርስ በማስመዝገብ ከአፍሪካ አንደኛ ናት - ዘጠኝ ቅርሶች በማስመዝገብ። ስምንት ስምንት ቅርሶች በማስመዝገብ የሚከተሏት ደቡብ አፍሪካ፣ ቱኒዚያ እና ሞሮኮ ናቸው። ጎረቤት ኬንያ ደግሞ አራት ቅርሶች ብቻ ነው ያስመዘገበችው፡፡
እ.ኤ.አ በ2007 ይፋ የተደረገውን ሃምሳ ምርጥ የዓለማችን ቱሪስት መዳረሻ ሀገሮች ዝርዝርን ስንመለከት ከአፍሪካ ግብጽ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሞሮኮና ቱኒዚያ ነበሩ የተካተቱት፡፡ ግብፅ 8.6 ሚሊዮን ቱሪስቶች ስታስመዘግብ ቱኒዝያ 6.5 ሚሊዮን አስመዝግባለች፡፡ በእርግጥ ባለፉት ሦስት አመታት ከተከሰተው የአረብ አብዮት ጋር ተያይዞ የቱሪስቶች ቁጥር ማሽቆልቆሉ አልቀረም፡፡

አገራቱ ሲረጋጉ ግን እንደገና ቁጥሩ አድጓል፡፡ በኢትዮጵያ ደግሞ በ2002 ዓ.ም የተመዘገበው የቱሪስት ቁጥር ግማሽ ሚሊዮን እንኳን አልደረሰም - 468,365 ነው፡፡ የባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከስድስት ዓመት በኋላ በ2012 ዓ.ም ኢትዮጵያን ከአፍሪካ አምስት ምርጥ የቱሪስት መዳረሻ ሀገራት አንዷ ለማድረግ አቅዷል፡፡ ሆኖም እቅዱ ከእነቱኒዝያ፣ ታንዛንያ እና ኬንያ አንጻር ሲታይ ገና እጅግ በጣም ብዙ ይቀረዋል፡፡
በሌላ በኩል መንግስት ተጨማሪ ሰባት ቅርሶች በዩኔስኮ ለማስመዝገብ በእንቅስቃሴ ላይ ነው፡፡ ከቅርሶቹም መካከል የመስቀል በአል እና ባሕረሐሳብ የተሰኘው የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ይገኙበታል፡፡ የሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ በደን ምንጠራና በሌላ የሰዎች ተጽዕኖ ከዓለም ቅርስነት የመፋቅ አደጋ አንዣቦበት እንደነበር ይታወቃል፡፡ ፓርኩን የመከለል እንቅስቃሴ በመጀመሩ ነው ከመሰረዝ የዳነው፡፡
የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን ለማስፋፋት መንግሥት ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ አምስት ክፍሎች ያሉት ብሔራዊ የቱሪዝም ልማት ፖሊሲ አዘጋጅቷል፡፡ የፖሊሲው ክፍል ሦስት፣ ቁጥር አራት “በዓለም አቀፍ የቱሪዝም ገበያ ፉክክር ውስጥ ብቁ ተወዳዳሪ ለመሆን የማስተዋወቅ ሥራን በመሥራት ጠንካራ የገበያ ትሥሥር” መፍጠር ወሳኝ መሆኑን ያወሳል፡፡

ተገቢ የፕሮሞሽን ሥራዎችን መስራት አስፈላጊ እንደሆነ ይጠቁማል - ፖሊሲው። በዚህም መሠረት የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፤ ዓለም አቀፍ ዐውደርእዮችን እንደ ዋነኛ የቅስቀሳ ዘዴ እየተጠቀመባቸው ይገኛል፡፡ ሚኒስቴር መ/ቤቱ ሥራዬ ብሎ በዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ቅርሶችንም ሆነ የተፈጥሮ መስህቦችን ሲያስተዋውቅ አይታይም፡፡ መገናኛ ብዙሃኑ በራሳቸው ጊዜ መጥተው ስለ ቅርሶቹና መስሕቦቹ ከሚዘግቡት በቀር በዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ለምን መስህቦችን አታስተዋውቁም በሚል የተጠየቁት በሚኒስቴሩ የሕዝብ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አወቀ ጤናው፤ “በዚህ መልኩ አናስተዋውቅም፡፡ ከዚያ ይልቅ በምናተኩርባቸው ሀገራት ያሉ ታዋቂ ፀሐፍትንና ሌሎች ተጽዕኖ ፈጣሪ ሰዎችን በመጋበዝ ስለ ኢትዮጵያ ቅርሶችና መስሕቦች እንዲጽፉ፣ እንዲናገሩ እናደርጋለን፡፡ በዓለም አቀፍ ዐውደርእዮች በመሳተፍም ሀገራችንን ይበልጥ እናስተዋውቃለን” ሲሉ መልሰዋል፡፡
በቱሪዝም ዘርፉ እንደ ድክመት ከሚጠቀሱ ጉዳዮች አንዱ በዘርፉ የሰለጠኑና የተካኑ ባለሙያዎች በበቂ ሁኔታ አለመኖር ነው፡፡ አቶ አወቀ በበኩላቸው፤ ሲቪል ሰርቪስ ሚኒስቴር በዘርፉ ብቃት ያላቸው ባለሙያዎችን መድቦ እየሰሩ መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡
አቶ አብዱ ከድር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለማስትሬት ዲግሪ ማሟያቸው እ.ኤ.አ በ2013 “Tourist Destination competitiveness of Ethiopia; The Tour operators perspective” በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናት ማጠቃለያ ላይ፤ “ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የቱሪዝም ዐውደርእይ ላይ ስትሳተፍ ከፖለቲከኞች ይልቅ ገበያ ሊያመጡ በሚችሉ የዘርፉ ባለሙያዎች ብትወክል ይበጃታል” ብለዋል፡፡ መካከለኛው ምስራቅ በተለይም የዓረቡ ዓለም የተዘነጋ የኢትዮጵያ የቱሪዝም ገበያ ክልል እንደሆነም በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡ ሚኒስቴሩ አምና ባሳተመው መጽሔት ላይ ኢትዮጵያን ከሚጐበኙ ዓለም አቀፍ ቱሪስቶች ውስጥ 51.2 በመቶ የሚሆኑት የአሜሪካ፣ ቻይና፣ እንግሊዝ፣ ጀርመን፣ ኬንያ፣ ጣሊያን፣ ሳኡዲ አረቢያ፣ ሕንድና ፊንላንድ ዜጐች መሆናቸውን ያመለክታል፡፡
ችግሩ ግን እነዚህ ቱሪስቶች በሚጎበኟቸው ስፍራዎች አብዛኛውን ጊዜ የሚቀበሏቸው አስጐብኝዎች በቂ እውቀትና ልምድ የሌላቸው ከማስጎብኘት ይልቅ ከማገት የሚስተካከል ሚና የሚጫወቱ ወጣቶች እንደሆኑ ጥናቶች ያሳያሉ። በዚህም የተነሳ በዓመት ግማሽ ሚሊዮን እንኳን ያልደረሱት የኢትዮጵያ ጎብኚዎች በአገሪቱ ውስጥ ያላቸው ቆይታ በጣም ውሱን ነው፡፡ እስራኤል በቱሪስት ብዛት ቀዳሚ ከሆኑትን ፈረንሳይ እና አሜሪካ ጋር ልትወዳደር አትችልም፡፡ ነገር ግን የቆይታ ጊዜአቸውን በማራዘም ከቱሪዝም ዳጎስ ያለ ገቢ እንደምታገኝ መረጃዎች ይጠቁማሉ። አንዲት ትንሽዬ የእስራኤል ከተማን በቅጡ ጐብኝቶ ለመጨረስ ቀናት እንደሚፈጅ ይነገራል። ኢትዮጵያም የእስራኤልን ፈለግ የመከተል ብርቱ ጥረት ልታደርግ ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎችና መንገዶችን በስፋት በመገንባት የጉብኝት ስፍራዎችን ለማብዛት መትጋትን ይጠይቃል፡፡
ከዚሁ ጐን ለጐን የኢንተርኔት አገልግሎቶችን በተለይ የቱሪዝም መስህብ በሆኑ ስፍራዎች ማስፋፋት ብቻ ሳይሆን ፈጣንና ቀልጣፋ ማድረግም የግድ ነው፡፡ ባለፈው ሰኔ ወር መጨረሻ፣ የኮንሶ አካባቢ ዓለም አቀፍ መካነ ቅርስ የሆነበት አንደኛ ዓመት ሲከበር፣ በርካታ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች የኢንተርኔት አገልግሎት ለማግኘት አርባምንጭ ድረስ ለመጓዝ መገደዳቸውን ታዝቤአለሁ፡፡
በቂ የቱሪዝም እውቀትና ልምድ የሌላቸው አስጐብኝዎች፣ መስተንግዶአቸው እንደነገሩ የሆኑ ሆቴሎች፣ ደካማና ፈዛዛ እንቅስቃሴ ይዘን ከአፍሪካ ምርጥ አምስት የቱሪዝም መዳረሻ አገራት አንዱ ለመሆን ማሰብ ከህልምነት አያልፍም፡፡
የቱሪዝም ኢንዱስትሪው በአንድ ወገን ጥረትና ትጋት የታሰበበት ደረጃ ላይ ሊደርስ አይችልም። ከግሉም ሆነ ከመንግሥት ዘርፍ የለያዩ ወገኖች ተዋናይ የሆኑበት ሰፊ ክፍለ ኢኮኖሚ በመሆኑ የተቀናጀ የጋራ ስራን ይፈልጋል፡፡ ከልብ መትጋትን ይጠይቃል፡፡ ያኔ የታቀደውም ሆነ የታለመው ሊሳካ ይችላል፡፡ በተለይ ደግሞ ራሳችንን በማስተዋወቁና በመሸጡ በኩል እጅግ ብዙ የቤት ሥራ እንዳለብን ማወቁ ተገቢ ነው፡፡

የውጭ ንግድ ፈቅ አላለም፤ ባለበት ደንዝዞ ቆሟል - የንግድ ሚኒስቴር መረጃ።
የግል ኢንቨስትመንት ተዳክሟል፤ ድርሻው በግማሽ ቀንሷል - የIMF መረጃ።
የአገሪቱ የባንክ ብድር፣ 90% ወደ መንግስት ይሄዳል - የአለም ባንክ ሪፖርት።
“ትልልቅ ፕሮጀክቶች በውጭ ምንዛሬ እጥረት እየተቀየዱ የሚሄዱበት እድል ሰፊ ነው” … የኤክስፖርት ገቢ መዳከሙን በመግለፅ ይህን የተናገሩት የንግድ ሚኒስቴር ሃላፊዎች ናቸው። ያሳስባል፣ እውነታቸውን ነው። ነገር ግን፣ ትልቁና አሳሳቢው ነገር፣ የመንግስት ፕሮጀክቶች መስተጓጎላቸው አይደለም። የውጭ ንግድ መዳከም፣ ጠቅላላ በአገር ኢኮኖሚና በዜጎች ኑሮ ላይ ተጨማሪ ችግር እንደተደቀነ የሚጠቁም ምልክት ነው። ደግሞስ፣ የመንግስት ገናናነት እየገዘፈ፣ የግል ኢንቨስትመንት እየቀጨጨ፣ እንዴት ጥሩ ውጤት ይገኛል ብሎ መጠበቅ ይቻላል?
አሳዛኙ ነገር፣ መንግስት ራሱን በራሱ ጠልፎ እየጣለ መሆኑን አለመገንዘቡ ነው። መንግስት “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ” ውስጥ የዘረዘራቸውን ትልልቅ ፕሮጀክቶች ለማሳካት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ያስፈልገዋል። ግን ምን ዋጋ አለው? ዋነኛ የውጭ ምንዛሬ ምንጭ የሆነው የግል ኢንቨስትመንት እየቀጨጨ የመጣው፣ “በእድገትና ትራንፎርሜሽን እቅድ” ሳቢያ ነው። ተግባራዊ የተደረጉ የመንግስት እቅዶች፣ የኤክስፖርት ገበያውንና የውጭ ምንዛሬ ምንጮችን እንዴት እየጎዱ እንደሆነ ለማሳየት እሞክራለሁ።
በእርግጥ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ የሚስተጓጎል ፕሮጀክት የለም ብለዋል። የሕዳሴ ግድብ ግንባታ በጭራሽ አይጓተትም ያሉት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም፣ ሌሎቹ ትልልቅ ፕሮጀክቶች ደግሞ በውጭ ብድር የሚካሄዱ በመሆናቸው የውጭ ምንዛሬ እጥረት እንደማያሳስብ ለመግለፅ ሞክረዋል።
እንዲያም ሆኖ፣ ከኤክስፖርት የሚገኘው ገቢ የታሰበውን ያህል እንዳልተሳካ አልካዱም። ቢሆንም፣ ይህንን ጉድለት የሚሸፍን ነገር ተገኝቷል። ከተለያዩ ምንጮች ወደ ኢትዮጵያ የተላከው የውጭ ምንዛሬ ከተጠበቀው በላይ ሆኗልና። ለነገሩ፣ በየአገሩ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በየአመቱ የሚልኩት ገንዘብ ቀላል አይደለም። በአመት ከ3 ቢሊዮን ዶላር በላይ እየላኩ ነው። ከኤክስፖርት ከሚገኘው ዶላር ይልቅ፣ ከዳያስፖራ የሚመጣው በልጧል። በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ለቤተሰብና ለዘመድ የሚልኩት ገንዘብ መጨመሩ ጥሩ ነው። ነገር ግን፣ የኤክስፖርትን ጉድለት ይሸፍናል በሚል የሚያፅናና አይደለም - በእጅጉ የሚያሳስብ እንጂ።
ከሳምንት በፊት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም፣ በውጭ ምንዛሬ እጥረት የመንግስት ፕሮጀክቶች እንደማይስተጓጎሉ ቢገልፁም፤ ከምር ሳያሳስባቸው የቀረ አይመስለኝም። በዚያው ሳምንት የንግድ ሚኒስቴር ሃላፊዎች ከክልል መስተዳድር ተወካዮች ጋር ተሰብስበው የተነጋገሩበት ዋና ርዕሰ ጉዳይ፣ በውጭ ምንዛሬ እጥረት ነው። ወደ ውጭ የሚላኩ የእርሻና የፋብሪካ ምርቶች፣ በጥራትና በብዛት እየቀረቡ አይደለም በማለት የተናገሩት የንግድ ሚኒስቴር ሃላፊዎች፣ “ትልልቅ ፕሮጀክቶች በውጭ ምንዛሬ እጥረት እየተቀየዱ የሚሄዱበት እድል ሰፊ ነው” በማለት አሳሳቢነቱን ገልፀዋል።
ከአመት አመት የኤክስፖርት እድገት እየተዳከመ መምጣቱን የሚክድ ይኖራል ብዬ አልገምትም። አሁን ደግሞ፣ ከነጭራሹ ቅንጣት እድገት አልታየም። እንዲያውም የኤክስፖርት ገቢ ቀንሷል። በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ውስጥ ከተዘረዘሩት “ግቦች” ጋር ሲነፃፀርማ፣ በእጅጉ ወደኋላ ቀርቷል። የእቅዱ ግማሽ ያህል እንኳ አልተሳካም።
በእቅዱ የመጀመሪያ ዓመት በ2003 ዓ.ም፣ ሁለት ቢሊዮን ዶላር የነበረውን የኤክስፖርት ገቢ በአንድ ቢሊዮን ዶላር ለማሳደግ (3 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ) ቢታሰብም፣ የእቅዱ 75 በመቶ ብቻ ነው የተሳካው። ቀላል እድገት ነው ማለቴ አይደለም። 2.75 ቢሊዮን ደርሷል። በቀጣዩ ዓመት ግን፣ እድገቱ ተዳክሟል። በ“ኦሪጅናሉ” እቅድ መሰረት፣ የኤክስፖርት ገቢ በ2004 ዓ.ም ወደ አራት ቢሊዮን ዶለር የሚጠጋ ይሆናል ተብሎ ነበር የታሰበው። በተግባር የተገኘው ገቢ ግን 3.15 ቢ. ዶላር ነው። ከመነሻው አመት ጋር ሲነፃፀር በሁለት ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ገቢ ለማግኘት ቢታቀድም፣ በተግባር የተገኘው እድገት 1.2 ዶላር ገደማ ነው። እናም እቅዱ 60 በመቶ ብቻ ነው የተሳካው ማለት ይቻላል።
አሁንም ኦሪጅናሉን እቅድ ካስታወስን፣ በ2005 ዓ.ም ከአምስት ቢሊዮን ዶላር በላይ የኤክስፖርት ገቢ ለማግኘት ታስቦ እንደነበር እናያለን። በተግባር የተገኘው ውጤት ደግሞ 3.1 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነው። የአመት አመት እድገቱ ተዳክሞ ከመቆሙም በላይ፣ የኋሊት መንሸራተት ጀምሯል። በ2002 ዓ.ም ከነበረው መነሻ አሃዝ ጋር ስናነፃፅረው፣ በሦስት ቢሊዮን ዶላር የላቀ እንዲሆን ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ 1.1 ቢሊዮን ዶላር ያህል ብቻ ነው የተሳካው። የእቅዱ 37% ብቻ ማለት ነው። ከአመት አመት የስኬቱ መጠን እየቀነሰ መሆኑን የምታስተውሉ ይመስለኛል።
ዘንድሮም የኤክስፖርት ገቢ ከሰባት ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ይሆናል ተብሎ በእድገትና ትራንስፎርሜሽ እቅዱ ውስጥ ተጠቅሷል። ሃሙስ እለት የወጣው የአይኤምኤፍ መግለጫ እንደሚያመለክተው ግን፣ የኤክስፖርት ገቢው 3.6 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ይሆናል ተብሎ ነው የሚጠበቀው።
እንግዲህ አስቡት፤ የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ ላይ የሰፈረው፣ በ2002 ዓ.ም ሁለት ቢሊዮን ዶላር የነበረውን የኤክስፖርት ገቢ፣ በ2006 ዓ.ም በአምስት ቢሊዮን ዶላር ይጨምራል የሚል እቅድ ነው። በእውን ይታያል ተብሎ የሚጠበቀው ጭማሪ ግን 1.5 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነው። የእቅዱ 33% ብቻ መሆኑ ነው።
የእቅዱ ስኬት ከአመት አመት እየቀነሰና እየተሸረሸረ የመጣው አለምክንያት አይደለም። የእቅዱ መዘዝ ከአመት አመት እየጨመረና እየተደራረበ ስመጣ ነው። ‘መዘዝ’ ስል፣ ያልታሰበና ያልተጠበቀ መመዝ ማለቴ አይደለም። በደንብ ታስቦበታል። ከዚያም አልፎ፣ የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ በይፋ ተዘርዝሯል። በአምስት አመታት ውስጥ በአገሪቱ ከሚካሄዱ የኢንቨስትመንት ስራዎች ውስጥ 67 በመቶ ያህሉ በመንግስት ፕሮጀክቶች፣ 33 በመቶ ያህሉ ደግሞ በግል ኢንቨስትመንት እንደሚሸፈን በ“እቅዱ” ውስጥ ተጠቅሷል። በሌላ አነጋገር፣ የመንግስት ፕሮጀክቶች፣ ከግል ኢንቨስትመንቶች በእጥፍ እንዲበልጡ ነው የታቀደው።
ድሮ እንደዚያ አልነበረም። ኢህአዴግ ስልጣን በያዘባቸው የመጀመሪያ አመታት፣ ከመንግስት ፕሮጀክቶች ይልቅ የግል ኢንቨስትመንት ድርሻ ይበልጥ ነበር - (የግል ኢንቨስትመንት 70 በመቶ የመንግስት ደግሞ 30 በመቶ)። መንግስት የነፃ ገበያ ኢኮኖሚን እገነባለሁ ቢልም፣ ቀስ በቀስ የግል ኢንቨስትመንት ድርሻ እየቀነሰ፣ በተቃራኒው የመንግስት ፕሮጀክቶች ድርሻ እየጨመረ መጥቷል። የዛሬ አስር አመት ገደማ ነው፣ የሁለቱ ድርሻ እኩል የሆነው (ሃምሳ በመቶ - ሃምሳ በመቶ)። የዚህን ጊዜም ነው፣ በመላው ዓለም ወደ ሶሻሊዝም ያዘነበሉ ናቸው ከሚባሉ አምሳ አገራት መካከል አንዷ ኢትዮጵያ መሆኗ የተገለፀው።
የቁልቁለት ጉዞው ግን በዚሁ አላቆመም። አይኤምኤፍ ሀሙስ እለት ባሰራጨው ዘገባ እንደገለፀው፣ የግል ኢንቨስትመንት ድርሻ ወደ 25 በመቶ እንደወረደና የመንግስት ፕሮጀክቶች ድርሻ 75 በመቶ እንደደረሰ ይገልፃል። በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ውስጥ ከተጠቀሰውም በላይ የከፋ መሆኑን ተመልከቱ። እንዲህ አይነት የመንግስት ገናናነት፣ በብዙ አገራት ውስጥ የለም። በእጅጉ ሶሻሊስታዊ የኢኮኖሚ አካሄድን ከሚከተሉ ሶስት የዓለማችን አገራት መካከል አንዷ ኢትዮጵያ ሆናለች የተባለውም በዚህ ምክንያት ነው። ነፃ ገበያ እንዲህ ነው እንዴ?
የመንግስት ፕሮጀክቶች ድርሻ እያበጠ፣ የግል ኢንቨስትመንት ድርሻ እየተደፈጠጠና እየቀጨጨ የመጣው፣ በተለያዩ ምክንያቶች ቢሆንም፣ ትልቁና ዋናው ሰበብ ግን ከባንክ ብድር ጋር የተያያዘ ነው። የባንክ ብድሮች ከአመት አመት ከግል ኢንቨስትመንት እየራቁ ወደ መንግስት ፕሮጀክቶች እንዲጎርፉ ተደርጓል። ከ20 አመታት በፊት፣ ከግማሽ በላይ የባንክ ብድሮች ለግል ኢንቨስትመንትና ለግል ቢዝነሶች የሚውሉ ነበሩ።
ግን ብዙም ሳይቆይ የባንክ ብድር አቅጣጫው ተቀይሮ፣ ወደ መንግስት ድርጅቶችና ፕሮጀክቶች መጉረፍ ጀመረ። በ2003 ዓ.ም፣ ከባንኮች አዲስ ብድር ውስጥ 70 በመቶ ያህሉ ለመንግስት ድርጅቶችና ፕሮጀክቶች እንደተሰጠ የሚገልፀው የአለም ባንክ ሪፖርት፣ ከዚያ ወዲህ ባሉ አመታትም የግል ድርጅቶች የሚያገኙት ብድር ይበልጥ እየቀነሰ እንደመጣ ያትታል። አሁን፣ ከባንኮች ብድር ውስጥ 90 በመቶ ያህሉን የሚወስዱት የመንግስት ድርጅቶችና ፕሮጀክቶች ናቸው። State Owned Enterprises are increasingly absorbing domestic banking sector credit. In the six-month period from June 2011 to December 2011, 71 percent of new loans were directed towards public enterprises. This share increased to 89 percent during the second half of 2012. A substantial share of the available foreign exchange is similarly diverted towards public investment. (የአለም ባንክ ሪፖርት Ethiopia Economic Update II፡ Laying the Foundation for Achieving Middle Income Status፡ June 2013 … ገፅ 24)
በዚህ መልኩ፣ ለግል ኢንቨስትመንት የሚውል የባንክ ብድር እየተንጠፈጠፈ፣ የግል ኢንቨስትመንት እየቀጨጨ ሲሄድ፣ የውጭ ምንዛሬ ገቢ እየቀነሰ መምጣቱን ምኑ ይገርማል? ከሞላ ጎደል በሸቀጦች ኤክስፖርት የሚገኘው ገቢ፣ በግል ድርጅቶችና ኢንቨስትመንቶች አማካኝነት የሚመጣ ነዋ። ታዲያ፣ መንግስት ራሱን በራሱ ጠልፎ አልጣለም ትላላችሁ? በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ውስጥ የተዘረዘሩትን ትልልቅ ፕሮጀክቶች ለማከናወን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ያስፈልገዋል። ነገር ግን፣ “እቅዱ” ራሱ፣ የውጭ ምንዛሬ ምንጭ የሆኑ የግል ኢንቨስትመንቶችን የሚደፈጥጥና የሚያቀጭጭ ነው።

 

ዓለም አቀፍ ጉባኤው፤ ሲኖዶሱ የመንፈሳዊ ኮሌጁን ችግር እንዲፈታ አሳሰበ
የክልል መንግሥታት የወረዳ ባለሥልጣናት÷ የቤተ ክርስቲያን ሕንፃ እንዳይታነፅ፣ የመካነ መቃብር፣ የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት መስጫ ቦታዎች እንዳይፈቀዱ፣ የቦታ ይዞታ ባለቤትነት በሕግ እንዳይረጋገጥ፣ ምእመናን ሥርዐተ አምልኮአቸውን በሰላምና በነጻነት እንዳይፈጽሙ፣ መብታቸውን ሲጠይቁም አፋጣኝና አግባብነት ያለው ፍትሕ እንዳያገኙ በማድረግ ተጽዕኖና በደል እያደረሱብኝ ነው ስትል የኦርቶዶክስ ቤ/ክርስትያን ወቀሰች፤ አቤቱታዋም በጥንቃቄ ታይቶ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጣት አሳሰበች።
ቤተ ክርስቲያኒቱ ከጥቅምት 4 ቀን ጀምሮ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ስታካሂድ በቆየችውና በዛሬው ዕለት እንደሚጠናቀቅ በሚጠበቀው ዓለም አቀፍ የመንበረ ፓትርያርክ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ ላይ፣ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተወካዮች ‹‹የብዝኃነት አያያዝ፣ አክራሪነት/ጽንፈኝነት ዝንባሌዎቹና መፍትሔዎቹ›› በሚል ርእስ ጽሑፍ አቅርበዋል፡፡ ‹‹የሃይማኖት መቻቻል›› በሚለው የአጠቃላይ ጉባኤው መርሐ ግብር ላይ በቀረበው በዚህ ጽሑፍ÷ ሌሎች አገሮች ብዝኃነትን ይዞና አቻችሎ አንድነትን ለማስቀጠል ተግዳሮት እንደኾነባቸው፣ የብዝኃነት ተምሳሌትና መገለጫ በኾነችው ኢትዮጵያ ግን በየጊዜው ወደ አገሪቱ የገቡ ሃይማኖቶች፣ በሰላም የተቀባበሉበትና በመገናዘብ የኖሩበት ጥልቅ ትርጓሜና ታሪክ እንዳለው ተገልጧል፡፡
ጽሑፉን ተከትሎ በነበረው ውይይት በሰሜን ወሎ፣ በምዕራብ ወለጋ ሦስት ዞኖች፣ በጋሞጎፋ ሦስት ወረዳዎች፣ በሶማሌ ዘጠኝ ዞኖች፣ በደቡብ ጎንደርና በወላይታ ኮንታ በዴሳ ወረዳ የሌላ እምነት ተከታይ በኾኑ የመንግሥት ባለሥልጣናት በቤተክርስቲያኒቱ ላይ ይፈጸማሉ የተባሉ የመብት መደፈሮች፣ የአስተዳደር፣ የፍትሕና የጸጥታ አካላት አድልዎች በሀገረ ስብከቶቹ ሊቃነ ጳጳሳት በዝርዝር ተሰምተዋል፡፡
ሊቃነ ጳጳሳቱ እንዳስረዱት÷ ለዞን መስተዳድር አካላት ውሳኔና መመሪያ የማይገዙ፣ የሌላ እምነት ተከታይ የኾኑና ሥልጣናቸውን ተጠቅመው ቤተ ክርስቲያኒቱን በፊውዳልነትና ነፍጠኛነት እየከሰሱ፣ ይዞታዋ እንዲነጠቅ ሕዝብን በበቀል ስሜት የሚያነሣሱ፣ በአማኞች ላይ አካላዊ ሥቃይና ሥነ ልቦናዊ ጫና በማድረስ ለመፈናቀልና ለሞት የሚዳርጉ፣ የሕዝቡን፣ የአገልጋዮችንና የሃይማኖት አባቶችን ጩኸት የማይሰሙ የወረዳ ባለሥልጣናት ጥቂቶች አይደሉም፡፡
በት/ቤት በአንገታቸው ማተብና መስቀል ያሠሩ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ተማሪዎች፣ ‹‹ከበላይ የመንግሥት አካል መምሪያ ተላልፎልናል፤ በሸሪዓ ሕግ ሴቶች ራሳቸውን እንዳይከናነቡ፣ ክርስቲያኖች ማተብና መስቀል እንዳያስሩ ተከልክሏል›› በሚሉ መምህራንና የፖሊስ አባላት ማተባቸው ከአንገታቸው ይበጠሳል፤ በጸሎተ ቅዳሴ ላይ ያሉ ምእመናን ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ በማስወጣት፣ ጸሎተ ቅዳሴው እንዲስተጓጎልና በበዓላት ቀን ሥራ እንዲሠሩም ይገደዳሉ፡፡ በሞትም በሕይወትም መደጋገፍ በሚታይባቸው ዕድሮችና በሕዝብ መጓጓዣዎች ሕዝቡ እንዳይረዳዳና እንዳይገለገል የወረዳ ዳኛ፣ ‹‹ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር አንድነት የለንም›› በማለት እስከ 80 ዓመት የቆየ ዕድር እንዲፈርስና ማኅበራዊ ግንኙነቶች እንዲታወኩ ምክንያት መሆኑ በስብሰባው ላይ በምሬት ተነግሯል፡፡
‹‹አንድ ሰው እግሩን እሳት እየበላው ቻል ይባላል? መቻቻል እስከ ምን ድረስ ነው?›› ሲሉ የጠየቁት የሰሜን ወሎ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቄርሎስ ‹‹እንድንቻቻል አድርጉን፤ እንችላለን›› ሲሉ የሚኒስቴሩን ተወካዮቹ አሳስበዋል፡፡
የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተወካዮች በውይይቱ ላይ ክርስትና በአራተኛው መቶ ክ/ዘመን ወደ ኢትዮጵያ መግባቱን የተናገሩ ሲሆን ሊቃነ ጳጳሳቱ መረጃው የተሳሳተ መሆኑን ጠቁመው ማስተካከያ ሰጥተዋል፡፡ ‹‹ከቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮና ከመጽሐፍ ቅዱሱ ምስክርነት ጋር የሚጣረስ ነው፤ ክርስትናን የተቀበልነው ክርስቶስ ዐርጎ ዓመት ሳይሞላው፣ ሐዋርያትም ከኢየሩሳሌም ሳይወጡ በ34 ዓ.ም በጃንደረባው አማካይነት ከእግዚአብሔር ነው፤›› በማለት በቀጣይ የሚኒስቴሩ ተወካዮች በተመሳሳይ ርእሰ ጉዳይ በቤተ ክርስቲያኒቱ መድረኮች ተገኝተው ገለጻ ሲሰጡም፤ ክርስትና በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደገባ የሚጠቅሱትን አርመው እንዲቀርቡ መክረዋቸዋል፡፡
‹‹ክርስትና በአራተኛው መ/ክ/ዘ ወደ ኢትዮጵያ ስለመግባቱ የተናገሩት ዐፄ ኢዛና ክርስትናን በኦፊሴል ተቀብለው ያስፋፉበት ወቅት በመኾኑ ነው›› ሲሉ የተናገሩት የሚኒስቴሩ ከፍተኛ አማካሪ፤ በ34 ዓ.ም. ጃንደረባው እንደ ግለሰብ መቀበሉ ኢትዮጵያን ሊወክል ይችላል ተብሎ ከታመነ፣ ‹‹እኛ እናንተ ባላችሁት ለማስተካከል ችግር የለብንም፤ የተስማማችኹ ከኾነ በታሪክ መጻሕፍትም ሳይቀር እንዲስተካከል እናደርጋለን፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 27/2 ማንኛውም ሃይማኖት እምነቱን ለማስፋፋት ተቋማትን መመሥረት እንደሚችል፣ ለዚህም የቁጥር ገደብ እንዳልተቀመጠ ተወካዮቹ አውስተዋል፡፡
የተጠቀሱት በደሎችና ጥፋቶች በተጨበጠ ማስረጃ ተጠናክረው እንዲሰጧቸውና እነርሱን በተግባር በመፍታት በሂደት እንዲፈትኗቸው ያመለከቱት የሚኒስቴሩ ተወካዮች፣ ስሕተት በመንግሥትም በሃይማኖት አባቶችም ዘንድ እንዳለ፣ በታሪክ አጋጣሚ ወደ ኋላ በቀሩትና የመሠረተ ልማት ዝርጋታና ትስስር በሌላቸው ክልሎች ደግሞ ስሕተቱ እንደሚጎላ፣ ወቀሳውም እያንዳንዱ ቤተ እምነት በሁሉ ላይ የሚያሰማው እንደኾነ ጠቁመዋል፡፡
በሊቃነ ጳጳሳቱ ያልተነገሩ በየወረዳው ያሉ በርካታ ቅሬታዎችን መከታተሉን የሚኒስቴሩ ተወካዮች ገልጸዋል፡፡ እንደ ጥፋት ደረጃውም ርምጃ የተወሰደበት ሁኔታና ተቀጥተው የተለቀቁ አካላት ስላሉ፣ በሕግ የተያዙት ጉዳዮች በሕግ እንዲያልቁ ሊቃነ ጳጳሳቱ ጠንክረው እንዲከታተሉ ጠይቀዋል፡፡
በሌላ በኩል ‹‹ኮሽ ባለ ቁጥር ወደ ቃሊቲ መፍትሔ ስለማይሆን›› ሚኒስቴሩ ግንዛቤ ላይ መሥራትን እንደሚያስቀድም፣ በሃይማኖት ተቋማቱም ዘንድ አስተምህሮውን ጠንቅቀው ያወቁ ሰባክያን ብቻ መሰማራት እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡ ‹‹እዚህ ተገኝታሁ ያቀረባችሁት ሐሳብ በጣም ጠቃሚ ነው›› በማለት ተወካዮቹን ያመሰገኑት ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፣ ‹‹በየጊዜው መነጋገር ለሃይማኖትም ለጸጥታም የሚጠቅም ስለሆነ መማማሩ በአንድ ጊዜ የሚያበቃ ባይኾን ጥሩ ነው›› ሲሉ ውይይቱ እንዲቀጥል ያላቸውን ፍላጎት ገልጸዋል፡፡
በሌላ ዜና ዓለም አቀፍ ጉባኤው በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎችና በአስተዳደሩ መካከል በተማሪዎች አቀባበልና የምዝገባ ቀን፣ መምህራን ከኮሌጁ መኖርያ ቤቶች እንዲለቁ ከተላለፈው የአስተዳደሩ ትእዛዝና ከኮሌጁ ሌሎች የአሠራር ችግሮች ጋር ተያይዞ ሰሞኑን ዳግመኛ ላገረሸው ውዝግብ፤ በቅርቡ የሚካሄደው ቅ/ሲኖዶስ ኹነኛ መፍትሔ እንዲሰጠው መጠየቁ ተዘግቧል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ የሥነ - ከዋክብት ተመራማሪ በአንድ የገጠር ከተማ ይኖር ነበረ፡፡ የዚህ ሰው የሁልጊዜ ፈሊጥ ማታ ማታ ከቤቱ እየወጣ የሰማይ ላይ ከዋክብትን ማየትና የሰው ልጆችን ዕጣ -ፈንታና የተፈጥሮን አካሄድ መመርመር ነበር፡፡
ይህን ክህሎቱን ከጊዜ በኋላ የተረዱ የከተማይቱ ሰዎች ቀስ በቀስ ስለሱ አዋቂነት ማውራት ጀመሩ፡፡ ዋሉ አደሩና እየተከተሉት ዕጣ - ፈንታቸውን ይጠይቁት ያዙ፡፡
አንደኛው - “የሥነ - ከዋክብት አዋቂ ሆይ! የእኔ የወደፊት ዕጣ ምን ይሆን?” ሲል ጠየቀው፡፡
አዋቂ - “ያንተን የከዋክብት ፈለግ እንዳየሁት የመጨረሻ ዕልፈትህ ጠብ ውስጥ ገብተህ ነው፡፡ ያላሰብከው ሰው ነው የሚገድልህ” አለው፡፡
አንደኛው - “ታዲያ ምን ባደርግ ነው የሚሻለኝ?”
አዋቂ - “በምንም ዓይነት ጠብ አካባቢ አትገኝ”
ሌላ ተከታዩ ይመጣል፡፡
“አዋቂ ሆይ! የእኔስ ዕጣ ምን ይሆን?”
አዋቂ - “ኮከብህ የብልጽግና ነው፡፡ ነገር ግን ምቀኞች አሉብህ”
ተከታይ - “ታዲያ ምን ባደርግ ከእነዚህ ምቀኞች ተንኮል አመልጣለሁ?”
አዋቂ - “ደግ እየመሰሉ ከሚቀርቡህ ሰዎች ተጠንቀቅ”
እንዲህ እንዲህ እያለ በየጊዜው እየተከተሉ ዕጣ - ፈንታቸውን ለሚጠይቁት ሰዎች መልስ ሲሰጥና ሲመክር ሰነበተ፡፡
አንድ ማታ እንደተለመደው ከከተማው ዋና በር (ከተምበሪ) አልፎ ሄደ፡፡
ቀና ብሎ ዐይኖቹን ሰማዩ ላይ ተከላቸው፡፡ መመራመሩን፣ መጠበቡን፣ መፈላሰፉን ቀጠለ፡፡ ይህን የየከዋክብቱን አካሄድና እንቅስቃሴ እያየ፣ እንዳንጋጠጠ፣ መራመዱን ቀጠለ፡፡ ሳያስበው ከእግሩ ሥር ካለ አንድ ደረቅ ጉድጓድ ውስጥ ድንገት ጥልቅ አለ፡፡
እዚያ ጉድጓድ ውስጥ ሆኖ እንደወቀደ ያጓራና ያቃስት ገባ፡፡ አንድ ሰው በዚያ አቅራቢያ ሲያልፍ የዚያን የሚያስጓጉር አዋቂ ድምጽ ሰማ፡፡ ወደ ጉድጓዱ አፍ ቀረበና ቁልቁል ተመለከተ፡፡ ሁኔታውን ካስተዋለ በኋላ፤
“ምን ልታደርግ እዚያ ገባህ?”
“ወድቄ ነው”
“እንዴት ይሄን የሚያህል ጉድጓድ አላየህም?”
“ሰማዩ ላይ በጣም አተኩሬ ስለበረ ነው”
“አይ ወዳጄ!” እንደዛ ታላቅ አዋቂ ነህ ብለን የተቀበልንህ ሰው፤ ሰማይ ሰማይ ስታይ እግሮችህ ወዴት እንሚወስዱህ እንኳ ካላወቅህ፤ እኔ እንደሚሰማኝ፤ አሁን ያለህበት ቦተ ተገቢ ቦታህ ነው!” አለው፡፡
* * *
ሰማይ ሰማይ ስናይ እግራችን ሥር ያለውን ነገር አንዘንጋ፡፡ ሰማዩን አተኩረን ስናይ ቀልባችን ሙሉ በሙሉ እሱ ላይ ብቻ ካረፈ፤ ከሥር እግራችንን የሚመታንን እንቅፋትና የሚያሰምጠንን ጉድጓድ አናየውም፡፡ ወደኃያላን መንግሥታት ስናንጋጥጥ የራሳችንን ህዝብ እንረሳለን፡፡ አልፈን ተርፈንም የሰዎችን ዕጣ-ፈንታ ስንናገር የራሳችንን ዕጣ-ፈንታ ሳናቅ እንዳንቀር እንጠንቀቅ!
ኃያላን መንግሥታት ሲሻቸው የበኩር ልጅ፣ ሲሻቸው የእንጀራ ልጅ ማድረግን ይችሉበታል፡፡ ኃያላን መንግሥታት “ሲሞቅ በማንኪያ ሲቀዘቅዝ በእጅ” ገንፎ መብላትን ያውቁበታል፡፡ መልዕክተኞቻቸውን ሲሻቸው በእርዳታ ሰጪ መልክ፣ ሲሻቸው በሚሲዮናውያንና በሃይማኖተኞች መልክ፣ ሲሻቸው በዲፕሎማት መልክ፤ ካልሆነም በቀጥታ ስለላ መልክተኞች - አሊያም በቱሪስት ወይም በፒስኮር መልክ ይልካሉ፡፡ ከከፋም የውስጥ ዐርበኛ ይቀጥራሉ፡፡ ላላ ያለ ካገኙም አገራቸው ድረስ ጋብዘው፣ አስተናግደው ሾመው፣ ሸልመው አንቱ ብለው ይቀባሉ፡፡
ያለ፣ የነበረ ወደፊትም የሚኖር ዘዴያቸው ነው፡፡ ይሄ ሁሉ ካልተሳካ የቁርጡ ቀን መጣ ማለት ነውና እንደ ኢራቅ የጦር ዘመቻ ያካሂዳሉ፡፡ እንደግሎባላይዜሽን አበጋዞች ሳይሆን እንደጥንቶቹ ቅኝ ገዢዎች- በግልጽ ወረራ ያካሂዳሉ፡፡
ከሁሉም ይሰውረን፡፡ ሲያወድሱ ሰማይ፣ ሲጥሉ እንጦር አውርደው ከትቢያ ይደባልቃሉ፡፡ የሁልጊዜ መሳሪያቸው ነው፡፡ እስካመቸናቸው እስካልቆረቆርናቸው ድረስ ያለእኛ በትክክለኛው የዕድገት መስመር ላይ ያለ አገር አይገኝም፡፡ “እንዲህ እያልሽ ውቴልሺን ሽጪ” እንዳለው ወሎ፤ የሚነግራቸው ጠፍቶ ነው፡፡ ለእነሱ የከፋን ለታ ግን ያለእኛ ኋላቀር፣ ያለእኛ ደንቆሮ፣ ያለእኛ ጦርነት ናፋቂ፣ ያለእኛ ረሃብተኛ፣ ያለእኛ መናጢ ደሃ የለም፡፡ ”እፀድቅ ብዬ ባዝላት ተንጠልጥላ ቀረች” ይሉናል፡፡
ከበረታን፤ “አላህንም አትክዳ፣ ሐረጓንም አትልቀቅ” እንዳሉት ጠቢብ ማሰብ አለብን፡፡
የኃያላኑን የቢዝነስ ኮሙኒቲ አይተን እኛ ምን እንሥራ ማለታችን ደግ ነገር ሆኖ፤ ከእዚህ ሁሉ በስተጀርባ ምን አለ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ምን ያህል ከልባቸው ነው? እነሱ፤ ለህዝባችን ይበጃል ያሉትን ማንኛውንም እኩይ ተግባር ከመፀፈም ወደኋላ ብለው ያውቃሉን? ብለን እንጠይቅ፡፡ ሁሉንም በትጋት በጉጉት - ዐይን እናስተውል፡፡
የፖለቲካ ፀሐፍት እንደሚነግሩን፤ “ሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎች የሚወድቁት ስህተት ስለሚሰሩ ሳይሆን ስህተታቸውን እንዴት እንደሚያርሙ ስለማያውቁ ነው፡፡ ይሄ የእኛም ችግር ነው፡፡ ሁለት ተጠቃሽ ባህሪዎቻችን፡- “ካፈርኩ አይመልሰኝ (Rigidity)”፣ እና “የአብዬን እከክ ወደእምዬ ልክክ (Blame shifting)” ናቸው፡፡ የሠራሁት ነገር ስህተት እንዳለበት ቢነገረኝም አልለቀውም፡፡ አንዴ አድርጌያለሁ ብያለሁ፡፡ ብያለሁ፡፡ ኃያላኑም ተናግረዋል፤ ማለት አይበጅም፡፡ በተቻለ መጠን በኃያላን ውዳሴ አለመማለል ብልህነት ነው! “ቅጥ - ያጣ መረጃ” ይዘን ነው እስካሁን የሄድነው ተብሏል፡፡ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ችግሮቻችን፣ የሚጨበጡትንና የማይጨበጡትን ጨምሮ፤ ስፍር - ቁጥር የላቸውም፡፡ በአንድ የድህነት ባኮ ከትተን ልንገላገላቸው መንገድ ከጀመርን ከራርመናል፡፡ አሁንም ግን በመጨለምና በንጨላጨል መካከል ነን፡፡
በሬዲዮ ጥያቄና መልስ ፕሮግራም “የሱዳን ዋና ከተማ ማን ትባላለች” ሲባል “አማርኛ ይሁንልኝ” …“የቆጡን አወርድ ብላ…” ጨርሰው ሲባል “ስፖርት ይሁንልኝ”፤ ዓይነት መልስ የሚመልስ ህብረተሰብ ይዘን እየዳከርን ነው፡፡ አገራችን፤ ላዩም ታቹም ይሄን መሳይ ነው!
በጭካኔ ፍትሕን ማምጣት (Brutal justice) እና የኢኮኖሚ አምባገነንነት (Economic Dictatorship) ቦታ ቦታ አላቸው፡፡ ጊዜ ጊዜም አላቸው፡፡ ለመተግበር ፍፁም ጥንቃቄን ይጠይቃሉ። ውጤታቸው ጠላት ማብዛት፣ ዜጋን ማስኮረፍ፣ ሕዝብን መሬት ውስጥ መክተት ሊሆን ይችላል፡፡ ሆደ - ሠፊና ለጋሥ አምባገነን መሆን (Benevolent Dictator) የዋዛ ነገር አይደለም፡፡ ህብረተሰብን በቅጡ ማሳመን ይሻል፡፡ በተለይም የተለያየ ሃይማኖት፣ ባህልና ብሔረሰብ ባለበት አገር እጅግ ከባድ አስተዳደራዊ ምሉዕነትን ይጠይቃል፡፡ የፈረንሳዩ መሪ ደጐል “ሶስት መቶ ስልሳ ዓይነት ዐይብ ያለውን ህዝብ ማስተዳደር ከባድ ነው” የሚለን ለዚህ ነው!

በኢትዮጵያ እና በናይጄሪያ የእግር ኳስ ጨዋታ በጋምቤላ ክልል ኚኝኛግ ወረዳ በደጋፊዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት የወረዳው አፈጉባኤ እና ወታደሮች እንደሞቱ ምንጮቻችን ገለፁ።
የደቡብ ሱዳን አዋሳኝ በሆነችው የኚኝኛግ ወረዳ ባለፈው እሁድ ኢትዮጵያና ናይጄሪያ በአዲስ አበባ ስቴዲየም ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ባደረጉት ጨዋታ፣ የናይጄሪያ ብሔራዊ ቡድን በማሸነፉ ደስታቸውን በጭፈራ በመግለጽ ላይ በነበሩ እና በድርጊቱ በተቆጡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ደጋፊዎች መካከል ግጭት ተፈጥሮ የኚኝኛግ ወረዳ አፈጉባኤና ከሁለት በላይ ወታደሮች እንደሞቱ ታውቋል፡፡
ችግሩ እንደተፈጠረ ከፌደራልና ከክልል የተውጣጡ ባለስልጣናት ቦታው ድረስ በመሄድ የማረጋጋት ስራ መሥራታቸውን ምንጮቻችን ጨምረው ገልፀዋል፡፡
የክልሉ ፕሬዝዳንት ሁኔታው ለማየት ወደ ስፍራው የሄዱ ሲሆን ስለ ጉዳዩ ፕሬዝዳንቱን በስልክ ለመጠየቅ ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡

          ትግራይ ክልል የማይአይኒ በተባለ ስፍራ የሚገኝ የኤርትራ ስደተኞች ካምፕ ውስጥ በተቀሰቀሰ ረብሻ የአንድ ሠው ህይወት ከጠፋ በኋላ፣ ተጠያቂ ናቸው የተባሉ ሰዎች እንደታሰሩ ምንጮቻችን አመለከቱ፡፡ ስደተኞች የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን በመቃወም ቢሮዎች የሰባበሩ ሲሆን፣ ወደ ጎንደር የሚወስደውም መንገድ ተዘግቶ ነበር፡፡
የረብሻው ምንጭ፣ ከሊቢያ ወደ ጣሊያን ሲጓዙ ለሞቱ በርካታ ኤርትራውያን የተዘጋጀ የመታሰቢያ ስነ ስርዓት እንደሆነ ምንጮቻችን ጠቅሰው ሻማ በማብራት የተጀመረው የመታሰቢያ ምሽት ወደ ተቃውሞ ረብሻ መቀየሩን አስታውሰዋል፡፡ በካምፑ ውስጥ የተፈጠረው ረብሻ ከቁጥጥር ውጭ ሆኗል በሚል ውሳኔ የፀጥታ ሀይሎች ጣልቃ እንደገቡ ምንጮቹ ጠቅሰው፤ በረብሻውና በግጭቱ የአንድ ሰው ህይወት እንደጠፋ ተናግረዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን (UNHCR) የህዝብ ግንኙነት ተወካይ አቶ ክሱት ገብረእግዚአብሔር፤ በሜዲትራኒያን ባህር ላምፑዱስ የተባለ ደሴት አቅራቢያ ህይወታቸውን ላጡ ወገኖች የሻማ ማብራት ስነ ስርአት እናደርጋለን በሚል የተጀመረው ፕሮግራም ለምን ወደ አመፅ እንዳመራ አናውቅም ብለዋል፡፡ ስደተኞቹ ወደ ጎንደር የሚወስደውን መንገድ እንደዘጉ አቶ ክሱት ጠቅሰው፣ የመንግስታቱ ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን እና አብረውን የሚሠሩ የሌሎች መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ላይ ተቃውሞ ተቀስቅሶ የቢሮ መስኮቶችና በሮች ተሠባብረዋል ብለዋል፡፡ ካምፕ ውስጥ የነበሩና አማራጭ ያጡ ወገኖች በሊቢያ በኩል ወደ ጣሊያን ለመግባት ሲሞክሩ ሞተዋል የሚል ሃሳብ በስደተኞች በኩል እንደተሰነዘረ አቶ ክሱት ጠቁመዋል፡፡
የመንግስታቱ ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን፣ በህጋዊ መንገድ ስደተኞችን ቢያጓጉዝ ኖሮ የበርካቶች ህይወት አይጠፋም ነበር በማለት በኮሚሽኑ ቢሮዎች ላይ ጥቃት እንደተፈፀሙ ሰምተናል ብለዋል-አቶ ክሱት፡፡ ስደተኞች ወደተለያዩ አገራት የሚጓጓዙት በኮሚሽኑ ፍላጎት ሳይሆን በተቀባይ አገራት በጎ ፈቃድ ነው ያሉት አቶ ክሱት፤ ኮሚሽኑ ለስደተኞች እንግልት ተጠያቂ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡