Administrator

Administrator

               ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር (አይ.ኤ.ኤ.ኤፍ) በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ለ2013 የዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ በሁለቱም ፆታዎች የሚፎካከሩ እጩዎችን ስም ሲያስታውቅ ከእጩዎቹ መካከል ሶስት የኢትዮጵያውያን አትሌቶች ተካትተዋል፡፡ መሃመድ አማን ፤ ጥሩነሽ ዲባባ እና መሠረት ደፋር ናቸው፡፡ አትሌት መሃመድ አማን በ800 ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ከመሆኑም በላይ በርቀቱ የዳይመንድ ሊግ አሸናፊ ለመሆን የበቃ እና በዓመቱ ካደረጋቸው 11 ውድድሮች አስሩን ያሸነፈ ነው፡፡ ዘንድሮ በ5ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃችው አትሌት መሰረት ደፋር በርቀቱ የዳይመንድ ሊግ አሸናፊ እንደሆነች ሲታወቅ በ3ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር የዓመቱን ፈጣን ሰዓት በማስመዝገብ ተሳክቶላታል፡፡ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ በበኩሏ በ10ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ከመሆኗም በላይ በ10 ኪሎሜትር የዓመቱን ፈጣን ሰዓት አስመዝግባለች፡፡

በኮከብ አትሌት ምርጫው በሁለቱም ፆታዎች ለመጨረሻ ምዕራፍ የሚደርሱትን ሶስት እጩ ተፎካካሪዎች ለመለየት በድረገፅ በሚሰጥ የድጋፍ ድምፅ ይሰራል፡፡ የዓለም የአትሌቲክስ ማህበረሰብን በማሳተፍ የሚከናወነው የምርጫ ሂደት ከተጀመረ ሶስት ቀን አልፎታል፡፡ ለሶስቱ የኢትዮጵያ ምርጥ አትሌቶች በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ድረገፅ (www.iaaf.org) አስፈላጊ የሆነውን ድምፅ በመስጠት ድጋፍ ሊሰጥ ይቻላል፡፡ እድሉ ለሚቀጥሉት ሶስት ሳምንታት ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡ በዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ ታሪክ ሶስት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ተሸላሚ ሆነው ያውቃሉ፡፡ እነሱም በ1998 እኤአ የተሸለመው ኃይሌ ገብረስላሴ፤ በ2004 እና በ2005 እኤአ አከታትሎ ያሸነፈው ቀነኒሳ በቀለ እና በ2007 እኤአ ላይ የተመረጠችው መሰረት ደፋር ናቸው፡፡

Saturday, 05 October 2013 10:56

እንግሊዝኛና አስተርጓሚ

...በጊዜው ያጋጥመን ከነበረው አስቸጋሪ ሁኔታ አንዱ የአስተርጓሚዎች በእንግሊዝኛ ቋንቋ ያለመብሰል ነው፤ ቀደም ብዬ እንዳስረዳሁት ከስንዴ፣ እንክርዳድ እንደማይታጣ ከአስተርጓሚዎችም መካከል አንዳንድ ደካሞች (ሞራለ ቢሶች) ሲኖሩ አብዛኛዎቹ ግን፤ በተማሩት የተጠቀሙበትና ጥሩ ኢትዮጵያዊነታቸውን ያሳወቁበት ስለሆኑ ውለታቸው የሚዘነጋ አይደለም፡፡ በዚህ ላይ ልገልፀው የፈለግሁት ግን በጊዜው እንግሊዝኛ እናውቃለን፣ ብለው በአስተርጓሚነት የተቀጠሩት ብዙዎች ሲሆኑ ባለችሎታ ሆነው የተገኙት ግን ጥቂቶች ነበሩ፡፡ ይሁን እንጂ ለመግደርደርና ዐዋቂ ናቸው ለመባል ያህል ባላቸው ቁንጽል ዕውቀት እንግሊዝኛ እናውቃለን የሚሉና በተለይ ከዚህ እንደሚከተለው፤
…የስ ሰር (YES SIR)፣ ኦል ራይት ሰር (ALL RIGHT SIR)፣ ቬርይ ጉድ ሰር (VERY GOOD SIR) በሚለው አነጋገር ብቻ አዘውትረው በመጠቀም የሚብለጠለጡም ነበሩ፡፡

እነዚህ አስተርጓሚዎች ነን የሚሉት ሰዎች፤ በነዚህ ሦስት ቃላቶች አዘውትረው የሚጠቀሙበት ምክንያት ሁለት ነው ይኸውም አንደኛው በተመልካች ዘንድ እንግሊዝኛ ያለመቻላቸው እንዳይታወቅባቸው ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ እንግሊዞቹ ለሚያቀርቡላቸው የቃል ጥያቄ ወይንም ለሚሰጧቸው ትእዛዝ ተቃዋሚ መልስ የሰጡ እንደሆነ (ኖ ሰር NO SIR) ያሉ እንደሆን ይህን ሊሉ የቻሉበት (የተቃወሙበትን) ምክንያት በእንግሊዝኛ አብራርቶ የማስረዳት ግዴታ ስለሚኖርባቸው፣ ከዚህ ሁሉ ጣጣ ለመራቅ የሚሻለው ነገሩ ቢገባቸውም ባይገባቸውም ጐላ ባለ ድምጽ የስ ሰር፤ ኦል ራይት ሰር ቬርይ ጉድ ሰር” ብሎ ዘወር ማለቱ የሚጠቅም ዘዴ መሆኑን ስላመኑበት ነው፡፡
ይሁን እንጂ ይህን የመሳሰሉት በእንግሊዝኛ ንግግር ደካማ የሆኑት አስተርጓሚዎች ትክክለኛ የሆነውን የሥራ ጉዳይ ስለሚመለከት ሁኔታ እንግሊዝኛውን ወደ አማርኛ ወይንም አማርኛውን ወደ እንግሊዝኛ በሚያስተረጉሙበት ጊዜ ንግግሩ አይሳካላቸው እንጂ “ትንሽ ዕውቀት መርዝ ነው” እንደተባለውና “የታሪክ ማስታወሻ” በተባለው መጽሐፍ በገጽ ፬፻፵ እንደተመለከተው ያልሆነውን ሆኗል ያልተባለውን ተብሏል በማለት፣ እንግሊዞቹንና እንግሊዝኛ የማናውቀውን ለማጋጨት፣ ባንዳንድ ሁኔታዎች ለማወናበድ አስችሏቸዋል፡፡ ከዚህ በስተቀር አማርኛና እንግሊዝኛ ቋንቋ ወዲያና ወዲህ እየሆኑ አንዳንድ አስፈላጊ ጉዳዮች በሚተረጐሙበትም ጊዜ ብዙ የሚያስቁ ሁኔታዎችን አድርሰው እንደነበረ በሚከተለው መስመር እገልጻለሁ፡፡
1ኛ፤ ሰዓት እላፊ (CURFEU) በሐምሌ ወር ፲፱፻፴፫ ዓ.ም አሥራ አንድ ሰዎች በሰዓት እላፊ ተይዘው 2ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስረው ካደሩ በኋላ በጊዜው ለነበረው የኦ.ኢ.ቲ.ኤ ፍርድ ቤት ቀርበው በሚጠየቁበት ጊዜ፣ የፍርድ ቤቱ ዳኛ (እንግሊዛዊው) የተከሰሱበትን የነጋሪት ጋዜጣ አዋጅ ተመልክተው “የተከሰሳችሁት ስለሰዓት እላፊ የወጣውን ዐዋጅ ተላልፋችሁ በመገኘታችሁ ነው፤ ጥፋተኛ ናችሁ አይደላችሁም?” ሲሉ ለተከሳሾቹ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡ አስተርጓሚውም ኬርፊው (CURFEU) የሚለውን የእንግሊዝኛ ቃል “ኩርፊያ” ብሎ በመተርጐም “እናንተ በኩርፊያ ወንጀል ተከሳችኋል፤ ጥፋተኞች ናችሁ አይደላችሁም?” ሲል በማስተርጐሙ፣ በአደባባዩ የነበሩት እንግሊዝኛ ቋንቋ የሚያውቁትና የማያውቁትም (ተከሣሾቹ) ጭምር አደባባዩን በሳቅ ከሞሉት በኋላ፣ ካሥራ አንዱ ተከሳሾች አንደኛው ባነጋገሩ ዝግ ያለው የባላገር ሰው ላስተርጓሚው በሰጠው መልስ “እኛ የታሰርነው በሰዓት እላፊ እንጂ በኩርፊያ አይደለም ደግሞስ ከዚያን በፊት የማንተዋወቅ ሰዎች በምን ተገናኝተን እንኳረፋለን፤” ጣሊያንም የፈጀን እርስዎን በመሰሉ አስተርጓሚዎች አሳሳችነት ነውና ይልቁንስ ነገሩን የጣሩልን” ሲል ስለተናገረ፣ ባደባባዩ ያለውን ሕዝብ ብቻ ሳይሆን እንግሊዛዊውን ዳኛ ጭምር አስቋቸዋል፡፡
2ኛ፤ የ2ኛ ፖሊስ ጣቢያ አዛዥ የሆኑት እንግሊዛዊ መኮንን በሰልፍ አቁመውን “ከሦስት ቀን በኋላ ግርማዊ ጃንሆይ ይገባሉ፤ በጥበቃው በኩል ጥንቃቄ ማድረግ አለባችሁ፤ ስለዚህም ጉዳይ ከበላይ መሥሪያ ቤት ፕሮግራም ይደርሰን ይሆናል፤ ያለበለዚያም በነገው ቀን በአውሮፕላን ወረቀት ስለሚጣል ትክክለኛውን ከዚያ መረዳት ይቻላል” ሲሉ ፀጥታውን ማስከበር አለባችሁ፤ ይህን ባትፈጽሙ አውሮፕላን ቦምብ ይጥልባችኋል ብሎ በማስተርጐሙ ሁላችንም በነገሩ ከተደናገጥንና ጥቂት ካሰብን በኋላ፣ ምንም እንግሊዝኛ ባንችል አስተርጓሚው የተሳሳተ መሆኑ ስለገባን ሁላችንም ስቀንበታል፤ ስህተቱን የተረዱት የጣቢያው አዛዥም ገስፀውታል፡፡
ምንጭ (በብርጋዲየር ጄነራል ሞገስ በየነ
“ጊዜ እና ፖሊስ” በሚል ርዕስ ከተዘጋጀ መጽሐፍ የተቀነጨበ፤ ከ1935-1963)

 

Saturday, 05 October 2013 10:29

የሞዴስ መዘዝ

ሞዴስ ወንዶችንም ለሞት ሊያበቃ ለሚችል በሽታ ይዳርጋል

ሴቶች የወር አበባቸውን የሚያዩበት ዕድሜ በአኗኗር ሁኔታ፣ በአመጋገብና በአካባቢያዊ ሁኔታዎች ሊለያይ የሚችል ቢሆንም በአብዛኛው ከ14 ዓመት ዕድሜያቸው ጀምሮ የወር አበባቸውን ያያሉ፡፡
ምቾት ባለበት አኗኗር ውስጥ የሚያድጉ ልጆች፤ ከዚህ ዕድሜ ቀደም ብለው የወር አበባቸውን ሊያዩ ይችላሉ፡፡ ይህ ቀደም ባሉት ዓመታት የነበረው የወር አበባ ማያ የዕድሜ ገደብ ዛሬ ዛሬ እየወረደ መጥቶ ታዳጊ ሴት ህፃናቱ፣ በዘጠኝና በአስር ዓመት ዕድሜያቸው ላይ የወር አበባ ማየታቸው እየተለመደ መጥቷል፡፡ ህፃናቱ የሰውነታቸው ዕድገት ፈጣን እንደመሆኑ ሁሉ የውስጣዊ አካላቸው ዕድገትና ለውጥ እንዲሁ ፈጣን ነው፡፡ እነዚህ ታዳጊ ህፃናት የወር አበባ ምንነትና ሒደቱ በሰውነታቸው ላይ ስለሚያስከትለው ተፈጥሮአዊ ለውጥ ግንዛቤ ባላገኙበት ዕድሜያቸው ላይ ይህ ክስተት ሲገጥማቸው ለከፍተኛ ድንጋጤና የሥነልቡና ጫና መዳረጋቸው የማይቀር ነው፡፡
ችግሩ እንዳይከሰት ቤተሰብ በተለይም እናቶች ለሴት ታዳጊ ልጆቻቸው ስለወር አበባ ምንነትና የወር አበባ በሚመጣ ጊዜ ሊደረጉ ስለሚገባቸው ጥንቃቄዎች እንዲሁም በወር አበባ ወቅት የግል ንጽህናን በአግባቡ መጠበቅ እጅግ አስፈላጊነ መሆኑን በጊዜ ማስተማርና ልጆቻቸውን ማዘጋጀት እንደሚኖርባቸው የዘርፉ ባለሙያዎች ይናገራሉ። ልጆቹ ያላወቁትና ይከሰትብኛል ብለው ያላሰቡት ነገር ሲገጥማቸው ከፍተኛ ድንጋጤና የሥነልቡና ችግር እንደሚደርስባቸውም ባለሙያዎቹ ይገልፃሉ።
ቀደም ባሉት ዘመናት እናቶች የወር አበባቸው በሚመጣበት ጊዜ ከነጠላና አሮጌ ቀሚሶች ቅዳጅ እየቆረጡ በሚያዘጋጇቸው ጨርቆች የወር አበባቸውን እየተቀበሉ ንጽህናቸውን ይጠብቁ ነበር። ጨርቆቹ እየታጠቡ ከአንድ ጊዜ በላይ አገልግሎት እንዲሰጡ ይደረጉ ነበር፡፡ አሁንም ቢሆን በአገራችን በርካታ አካባቢዎች ጥቅም ላይ እየዋለ ነው። ሴቶች የወር አበባቸው በሚመጣበት ወቅት የሚጠቀሙበትና ንጽህናቸውን የሚጠብቁበት መንገድ በአብዛኛው ባህላዊና ተለምዶአዊ ነው፡፡
ዘመናዊነቱ እየተስፋፋ፣ ቴክኖሎጂው እያደገ ሲሄድ ለሴቶች የወር አበባ መቀበያነት የሚያገለግሉና የሴቶቹና ንጽህና የሚጠብቁ ሞዴሶች ተሰርተው ገበያ ላይ መዋል ጀመሩ፡፡ የእነዚህ ምርቶች ገበያ ላይ መዋል ሴቶች በወር አበባ ወቅት የሚሰማቸውን የህመም እና ያለመመቸት ስሜት በእጅጉ ከመቀነሱ ባሻገር፣ ንጽህናቸው በአግባቡ ባልተጠበቁ ጨርቆች ሳቢያ የሚከሰቱ ችግሮችን ለማስቀረት አስችሏል፡፡
በፋብሪካ ደረጃ እየተመረቱ በጥቅም ላይ የሚውሉ ዘመናዊ የወር አበባ መቀበያ ፓዶችም ሆኑ የወር አበባ መቀበያ እራፊ ጨርቆቹ እጅግ አደገኛ የሆኑ ችግሮችን እንደሚያስከትሉ ጥናቶች ጠቁመዋል፡፡ “ጆርናል ኦፍ ኢንፌክሽን ዲዚዝ” ይፋ ባደረገው መረጃ፤ በወር አበባ መቀበያ ሞዴሶች ሳቢያ የሚራቡት አደገኛ ባክቴሪያዎች ከሴቶችም አልፈው ወንዶችን ለህልፈተ ህይወት እየዳረጉ ነው፡፡ በወር አበባ ወቅት በሚፈሰው ደም ውስጥ ጉሉኮስን የመሰሉ ለባክቴሪያ መራባት እጅግ አስፈላጊና ምቹ የሆኑ ነገሮች ይገኛሉ፡፡ እነዚህም በወር አበባ መቀበያ ሞዴስ ውስጥ በመግባት በቀላሉ ለመራባትና ለመሰራጨት ይችላሉ፡፡
ስታፈሎከሰስ የተባሉት እጅግ አደገኛ ችግር ሊያስከትል ለሚችል በሽታ ምክንያት የሚሆኑት ባክቴሪያዎች “ቶክሲክ ሽክ ሲንድረም” የተባለና እስከ ሞት ሊያደርስ የሚችል አደገኛ የፍትወተ አካል ኢንፌክሽን ይፈጥራሉ፡፡ በአብዛኛው ችግሩ የሚከሰተው ረዘም ላለ ጊዜ ጥቅም ላይ በሚውሉ (በወር አበባ ወቅት በሴቷ ብልት ላይ ረዥም ሰዓት በሚቆዩ) ሞዴሶች ወይንም ንጽህናቸው በአግባቡ ባልተጠበቀና በተደጋጋሚ በጥቅም ላይ በሚውሉ የወር አበባ መቀበያ ጨርቆች አማካኝነት መሆኑንም መረጃ አመልክቷል፡፡ ችግሩን እጅግ የከፋ የሚያደርገው ሌላው ጉዳይ፤ ይህ በሞዴሱ ሳቢያ የሚከሰተው አደገኛ በሽታ ለወንዶችም መትረፉ ነው፡፡ የችግሩ ሰለባ ከሆነች ሴት ጋር የግብረ ስጋ ግንኙነት የፈፀሙ ወንዶችም “በቶክሲክ ሾክ ሲንድረም” መጠቃታቸው አይቀሬ ነው፡፡ ችግሩ በወቅቱ ታውቆ ተገቢው ህክምና ካልተደረገለትም ለሞት ሊያደርስ እንደሚችል መረጃው አመልክቷል።
የወር አበባ መቀበያ ሞዴሶች በሴቷ ሰውነት ላይ መቆየት የሚገባቸው ከ3-4 ሰዓታት መሆን ይገባዋል ያለው መረጃው፤ ከዚህ ለበለጠ ጊዜ የሚቆይ ከሆነ ለባክቴሪያ መራቢያ ምቹ ሁኔታዎች ስለሚፈጠሩ ይኸው ስታፍሎኮከስ ኦርስ የተባለው ባክቴሪያ ይራባና ”ቶክሲክ ሾክ ሲንድረም” የተባለውን አደገኛ በሽታ ሊያስከትል እንደሚችል ገልጿል፡፡
ይህ እጅግ አደገኛና በግብረሥጋ ግንኙነት ሳቢያ ከአንዱ ወደ አንዱ የሚተላለፍ በሽታ ከመከሰቱ በፊት ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ እንደሚገባና ሴቶች በወር አበባ ወቅት የሚጠቀሙበትን ሞዴስ በንጽህና ሊጠቀሙበት እንደሚገባ “ጆርናል ኦፍ ኢንፌክሽን ዲዚዝ” አሳስቧል።

“በህይወት እስካለህ ደግ መስራት ጥሩ ነው”
በሆለታ ተወልደው ያደጉት አቶ ዘነበ ክንፉ ታፈሰ፣ ለትምህርት ወደ ራሽያ የሄዱት የዛሬ 22 ዓመት ገደማ ነው፡፡ ከልጅነታቸው ጀምሮ የፅሁፍ ፍቅር ነበራቸው፡፡ ነፃ የትምህርት እድል አግኝተው ወደ ሩሲያ የሄዱትም ኢንተርናሽናል ጆርናሊዝም
(ዓለም አቀፍ ጋዜጠኝነት) ለመማር ነበር፡፡
ትምህርታቸውን እስከ ዶክትሬት ደረጃ የተማሩት ፕሮፌሰር ዘነበ፤ በራሽያ ዩኒቨርስቲ ውስጥ እያስተማሩ ይገኛሉ፡፡ “ቢዝነስ አፍሪካ” የተሰኘ መፅሄት መስራችና ባለቤትም ናቸው፡፡ ጋዜጠኛ ግሩም ሠይፉ ለ14ኛው የዓለም ኦሎምፒክ ሻምፒዮን ሩሲያ በሄደ ጊዜ በሞስኮ ከተማ አግኝቶ አነጋግሯቸዋል፡፡ ስለሆለታ ትዝታቸው፣ ስለ ፅሁፍ ፍቅራቸው፣ ስለትምህርታቸውና ሙያቸው በስፋት አውግተዋል፡፡ እነሆ፡-


ጋዜጠኝነትን የተማሩት ራሽያ ቢሆንም ለጋዜጣ መፃፍ የጀመሩት ሆለታ እያሉ ነበር ሲባል ሰምቻለሁ…
እውነት ነው፡፡ ገና ታዳጊ ሳለሁ ጀምሮ እፅፍ ነበር፡፡ ስልክ አምባ እና ዜኒት የሚሉ የብዕር ስሞች ነበሩኝ፡፡ በእነዚህ ስሞች ፅሁፎቼን ለተለያዩ ጋዜጦችና የሬድዮ ፕሮግራሞች እልክ ነበር፡፡ ለመጀመርያ ጊዜ ፅሁፍ የወጣልኝ አዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ ነው፡፡ በኋላ ለሬድዮ ፕሮግራሞችና ለ“ሰርቶ አደር” ጋዜጣ ሁሉ መፃፍ ጀመርኩ፡፡ ፅሁፎቼ በማህበራዊ ችግሮች ዙርያ የሚያተኩሩ ነበሩ። አዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ የወጣውን የመጀመሪያ ፅሁፌን አራተኛ ክፍል ሆኜ ነው የፃፍኩት፡፡
ስለ እድገትዎ ይንገሩኝ…
የተወለድኩትና ያደግሁት ከአዲስ አበባ ወጣ ብላ በምትገኘው ሆለታ ከተማ ነው፡፡ በ1968 አካባቢ በከተማዋ ድርቅ ተከሰተ፡፡ የከተማው ነዋሪ ውሃ ፍለጋ አራትና አምስት ኪሎ ሜትር ይጓዝ ነበር፡፡ እኔም ከእናቴ ጋር ሄጄ ይህን ችግር አየሁ፡፡ የፃፍኩት ነገር … ለምንድነው ባለስልጣኖች የውሃ ጉድጓድ የማያስቆፍሩት የሚል ሃሳብ ይዟል፡፡ በጣም አጭር ፅሁፍ ነው፡፡ ግማሽ ገፅም አይሆንም፡፡ “የውሃ እጥረትን ለመፍታት የአካባቢው አስተዳደር መንቀሳቀስ አለበት” በሚል ነው የሚቋጨው፡፡ ፅሁፉን በጋዜጣው አድራሻ በፖስታ ቤት ላክሁት፡፡ ብዙም ሳይቆይ ነበር ጋዜጣው ላይ የወጣው፡፡
ከቤታችን ደጃፍ አንድ ባለሱቅ ነበር፡፡ መሃመድ ነው ስሙ፡፡ ስኳር ለመግዛት ወደሱ ሱቅ ስሄድ “ያንተ ስም ነው እንዴ እዚህ ጋዜጣ ላይ የወጣው?” ብሎ አሳየኝ፡፡ ለማንም እንዳትናገር ብሎ ፅሁፌ ያለበትን የጋዜጣውን ገፅ በ10 ሳንቲም ሸጠልኝ፡፡ አየህ የሆለታ እርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት ከቤታችን አቅራቢያ ነበር፡፡ በዚያ አትክልት በሚያፈሉበት ስፍራ የውሃ ጉድጓድ ቆፍረው ውሃ በማውጣት ይጠቀሙ ነበር። እዚያ ግቢ ውስጥ ውሃ አለ፡፡ እናቴ እና የከተማው ህዝብ ግን ረጅም ርቀት እየተጓዙ ውሃ ይቀዱ ነበር። የሚገርምህ ፅሁፉ ወጥቶ ብዙም ሳይቆይ ለሆለታ ከተማ ነዋሪ ውሃ ለማሰራጨት የጉድጓድ ቁፋሮ እንዲሰራ ባለስልጣኖች አዘዙ፡፡ ጉድጓድ ተቆፍሮ ውሃ ከወጣ በኋላ፣ ባንቧ ተሰርቶ ከተማው መሃል ውሃ ተገኘ፡፡ እኔም በዚሁ የውሃ ጉድጓድ፣ ውሃ ሻጭ ሆኜ መስራት ቻልኩ፡፡
ከልጅነትዎ አንስቶ ፀሐፊ የመሆን ፍላጐት ያሳደረብዎ ምንድነው?
እንደነገርኩህ ያኔ ገና አራተኛ ክፍል ብሆንም ብዙ አነብ ነበር፡፡ እቤታችን የተለያዩ ጋዜጦች ይመጣሉ፡፡ ጀርመናውያን ጐረቤቶች ስለነበሩን የእንግሊዝኛ ህትመቶችንም የማንበብ ዕድል ነበረኝ፡፡ የስነፅሁፍ ዝንባሌዬ ከፍተኛ ነበር፡፡ አንድ ጊዜ በአንድ ምሽት ባለ16 ገፅ ደብተር ሙሉ ግጥም ፅፌ ለአማርኛ አስተማሪያችን አሳየኋት፡፡ “ይሄ ግጥም የሚሆን አይደለም” ብላ አሳፈረችኝ። ግጥሙ ስለ ምን እንደሆነ ትዝ አይለኝም፡፡ የሆኖ ሆኖ ግጥሙን ትቼ ጋዜጠኛ ለመሆን አስብ ጀመር። ያኔ በጣም ከምወዳቸው ጋዜጦች አንዱ “ፖሊስ እና ርምጃው” ነበር፡፡ በጣም ቆንጆ ጋዜጣ ነው፡፡ አብዮት የተጀመረበት ጊዜ ስለነበር ብዙ ጋዜጦች እና መፅሄቶች ይወጡ ነበር፡፡ ሆለታ ከተማ ውስጥ የእጩ መኮንኖች ማሰልጠኛ፣ የእርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት እና ሌሎችም ተቋማት ነበሩ፡፡ በርካታ የውጭ አገር ዜጎችም ነበሩ፡፡ በዚህ ምክንያት ለመረጃ ቅርብ ነበርን፡፡ አባቴም አልፎ አልፎ ጋዜጦችን፣ መፅሃፍት እና መፅሄቶችን ያመጣልኛል። ሬድዮ እከታተላለሁ። ከተፈጥሮ ተሰጥኦዬ ጋር ይህ ሁሉ ሲጨመር ፀሃፊ ለመሆን ያነሳሳኝ ይመስለኛል፡፡
በወጣትነት ዘመንዎ ሆለታ ምን ትመስል ነበር?
የሆለታ ህዝብ እንደማንኛውም ኢትዮጵያዊ ነው። ልዩነቱ ሁሉም አይነት ብሄረሰብ የተሰባሰቡባት ከተማ መሆኗ ነው፡፡ ቅድም እንደነገርኩህ ሆለታ የእጩ መኮንኖች ማሰልጠኛ፣ የእርሻ ምርምር ኢንስቲትዩት፤ የመሳሪያ ግምጃ ቤት፤ የሙሉጌታ ቡሊ ቴክኒክ ትምህርት ቤት፤ የሱባ ደን ልማት፣ የወተት ሃብት ልማት… እነዚህ ሁሉ የመንግስት ድርጅቶች ነበሩባት፡፡ በኋላም እነ ሙገር በሆለታ መንገድ ላይ ተሰርተዋል፡፡ በእነዚህ የመንግስት ተቋማት ይሰሩ የነበሩት ከተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍሎች የተሰባሰቡ ናቸው፡፡ ኦሮሞው፣ አማራው፣ ትግሬው… ሁሉም ብሄር ብሄረሰብ ነበር፡፡ አትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆኑ የተለያዩ አገራት የውጭ ዜጎች እንዲሁም በርካታ አፍሪካውያን ነበሩ፡፡
ስራ የጀመርኩት እዚያው ሆለታ ውስጥ ነው፡፡ የመጀመሪያው ስራዬ የተለያዩ ሸቀጦችን መነገድ ነበር፡፡ 9ኛ ክፍል ሆኜ ነው የጀመርኩት። ለወታደሮችም እላላክ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ወደ ውትድርና ገባሁና ለአራት አመታት በአየር ወለድነት ሰለጠንኩ፡፡ በሰሜን እና በሰሜን ምዕራብ ዘምቼ፣ ብዙ ግዳጆችን ፈፅሜአለሁ፡፡ በውትድርና ዘመኔም መፃፉን አልተውኩትም፡፡ የሚገርምህ አንጋፋው ደራሲ በዓሉ ግርማ አለቃዬ ነበር። አስመራ ለሰራዊቱ በሚዘጋጅ “የጀግናው ገድል” የተባለ ጋዜጣ ላይ ፊደል ለቀማ (Proof reading) ስሰራ ማለቴ ነው። ያኔ እንግዲህ 19 አመቴ ነበር፡፡ በሰራዊቱ አባልነቴ ጋዜጣ በማቋቋምና የኪነት ቡድን በመመስረት ፈርቀዳጅ ሚና ተጫውቻለሁ፡፡ የኢትዮጵያ አየር ወለድ በኃይለስላሴ ጊዜ ፈርሶ በደርግ ዘመን በድጋሚ በሁርሶ ተቋቋመ፡፡ ከውትድርና የወጣሁት ወሎ አካባቢ በፓራሹት ስወርድ (ዝናብ ስለነበር) ወድቄ በመጐዳቴ ነው፡፡
ከውትድርና ወጥተው የት ገቡ?
ደቡብ ውስጥ ድርቅ ስለነበር በሻሸመኔ መልሶ ማቋቋም ተቋም ውስጥ ተቀጥሬ መስራት ጀመርኩ። አሁንም መፃፌን አልተውኩም፡፡ ባለኝ ትርፍ ጊዜ ሁሉ እየፃፍኩ በተለያዩ ህትመቶች ላይ ይወጣልኝ ነበር፡፡ በሬድዮም ይነበቡልኛል፡፡ የምፅፋቸው በአብዛኛው ትችቶች ነበሩ፡፡ ለምሳሌ “የባህር ዛፍ አጨዳ እና ሽያጭ” በሚል መሃል ሸዋ አካባቢ የሚካሄደውን የደን ጭፍጨፋ የሚመለከት መጣጥፍ ፅፌ ነበር፡፡ የባህር ዛፍ ጭፍጨፋው አደገኛ ችግሮች እንደሚያመጣ፤ የድርቅም ምክንያት እንደሆነ በመግለፅ የፃፍኩት ፅሁፍ፤ በ“ሰርቶ አደር” ጋዜጣ ላይ እንደታተመልኝ ትዝ ይለኛል፡፡
እንዴት ነው በራሽያ ነፃ የትምህርት እድል ያገኙት?
በሁለተኛ ደረጃ ብሄራዊ መልቀቂያ ፈተና 3.4 አመጣሁ፡፡ ውጭ ሄጄ መማር አለብኝ ብዬ አስብ ነበር፡፡ አሁን እንዴት እንደሆነ ባላውቅም ድሮ ስኮላርሺፕ የሚሰጡ አገራት ምርጫ ይቀርብልሃል። በውድድር ነው፡፡ የሦስት አገራት ምርጫ ተሰጠኝ። ከልጅነቴ ጀምሮ የምመኘውን የጋዜጠኝነት ሙያ ለመማር መረጥኩ፡፡ ለኢንተርናሽናል ጆርናሊዚም ነፃ የትምህርት እድል የነበራቸው አገራት ደግሞ ራሽያ፣ ቻይናና ሃንጋሪ ነበሩ፡፡ ሶስቱንም ሞላሁ፡፡ በመጀመርያ ቻይና ደረሰኝ፡፡ ሳይታሰብ ግን በዚያ አገር ብጥብጥ ተነሳ፡፡ ቻይናን የመረጥኩት ትልቅ አገር ነች በሚል ነበር፡፡ ከዚያ ራሽያ ደረሰኝና ከሌሎች ተማሪዎች ጋር ለፈተና ተቀመጥን፡፡ ፓትሪስ ሉምቡባ ዩኒቨርስቲ ነበር የተመደብነው፡፡ ሰባ ተማሪዎች ተወዳድረን ሁለት ልጆች ፈተናውን በማለፍ እድሉን አገኘን፡፡
ከ22 ዓመታት በፊት ሞስኮ ሲገቡ የአገሪቱ ሁኔታ ምን ይመስል ነበር?
ገና አብዮቱ ባይጀመርም በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የለውጥ ንቅናቄዎች እየተስተዋሉ ነበር፡፡ ፕሮስትሬይካና ግላሽኖስት (ግልፅነትና ተጠያቂነት) …የጎርባቾቭ የተሃድሶ እቅድ ተጀምሯል፡፡ ትርምሱ ታዲያ ለጋዜጠኛ ሰርግና ምላሽ ነበር፡፡ እኛ በወቅቱ ቋንቋ እየተማርን ቢሆንም እዚያው በገዛሁት ካሜራ ግርግሮችን ፎቶ እያነሳሁ እሰበስብ ጀመር፡፡ በኋላም ቪድዮ ካሜራ ገዝቼ በከተማዋ የሚታዩ የለውጥ ንቅናቄዎችን እቀርጽ ነበር፡፡ ይሄን የማደርገው ለሚዲያ ለመዘገብ ሳይሆን የራሴን የጋዜጠኝነት ስሜት ለማርካትና መረጃ መሰብሰብ ስለምወድ ነው፡፡ እንደስራ ልምምድም መሆኑ ነው፡፡ በኋላ ላይ “ሞስኮ ታይምስ” ለተባለ ጋዜጣ ሁላችንም መስራት ጀመርን፡፡ በነፃ ሳይሆን እየተከፈለን፡፡ ሞስኮ ውስጥ በአማርኛ ቋንቋ የሚሰራጭ ሬድዮ ጣቢያ ስለነበር እዚያም እሰራ ነበር፡፡ ዜና ማንበብ፤ ደብዳቤዎችን አንብቦ ምላሽ መስጠት ነበር ስራዬ፡፡ በ“ሞስኮ ታይምስ” ጋዜጣ ላይ ደግሞ በተለያዩ ጉዳዮች ዙርያ እፅፍ ነበር፡፡ የመጀመርያው ፅሁፌ ትዝ ይለኛል፡፡ የአፍሪካ ችግሮች ላይ የሚያተኩር ነበር፡፡ ከዚያም ኢትዮጵያን ማስተዋወቅ ጀመርኩ… ስለ ኢትዮጵያ በዓላትና፤ ስለ ባህል ብዙ ፅፌአለሁ፡፡ አብዛኞቹን በራሽያ ቋንቋ የፃፍኳቸው ቢሆንም በእንግሊዝኛም እየፃፍን ክፍያ እናገኝ ነበር፡፡
የትምህርቱስ ነገር?
ኢንተርናሽናል ጆርናሊዝም ለአምስት አመት ተምሬ በባችለር ዲግሪ ተመርቄአለሁ፡፡ ለዲግሪ ማሟያ የፃፍኩት የጥናት ወረቀት በኢትዮጵያ ፕሬስ አጀማመር እና ህጎች ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ በአጠቃላይ የሶሻል ሳይንስ ባለሙያ ነኝ፡፡ ማስትሬቴን በራሽያ ታሪክ፣ ፒኤችዲዬን ደግሞ በዓለም አቀፍ ግንኙነትና ዲፕሎማሲ ላይ ነው የሠራሁት፡፡ በኢንተርናሽናል ፊልም ሁለተኛ ማስትሬት ዲግሪም አግኝቻለሁ፡፡
መቼ ነው የፕሮፌሰርነት ማዕረግ ያገኙት?
በ2001 እ.ኤ.አ ላይ ነው ሙሉ ፕሮፌሰር የሆንኩት፡፡ በዋናነት የማስተምረው በራሽያ ዩኒቨርሲቲ ነው፡፡ ዓለምአቀፍ ጋዜጠኝነትና በአገራት የውጭ ግንኙነት ፖሊሲዎች ውስጥ እንዴት መስራት እንደሚቻል አስተምራለሁ፡፡ በተለያዩ አገራት እየተጋበዝኩም ሌክቸር እሰጣለሁ፡፡ በአጠቃላይ በ59 የዓለም አገራት ተዟዙሬ ሠርቼአለሁ፡፡ በባንግላዲሽ መገናኛ ብዙሐን ላይ አንድ መጽሐፍ አሳትሜያለሁ፡፡ አምና “የአፍሪካና የአረብ አብዮት” በሚል ርዕስ ሌላ መፅሃፍ ፅፌአለሁ፡፡ ባለፉት 5 ዓመታት በተለያዩ ዓለም አቀፍ ችግሮች ላይ ያተኮሩ፣ ከተለያዩ ምሁራን ጋር በትብብር የተዘጋጁ ከ49 በላይ መጽሐፍትና የጥናት ፅሁፎች ለህትመት በቅተውልኛል፡፡
“ቢዝነስ አፍሪካ” የተባለ መጽሔት እንደሚያሳትሙ ሰምቻለሁ፡፡ ስለዚህ ዓለም አቀፍ መፅሄት ይንገሩኝ…
መጽሔቱ የፖለቲካ ነው፡፡ በሦስት ቋንቋ ነው የምንጽፈው፡፡ በዋናነት የቻይና-አፍሪካንና የራሽያ-አፍሪካን ግንኙነትን ይዳሰሳል፡፡ ከፍተኛ አንባቢ ያለው ድረገጽም አለው፡፡ ለመጽሔቱ ቃለምልልስ የምናደርገው ከትላልቅ ኩባንያ ዳሬክተሮች፣ ሚኒስትሮች፣ ከተለያዩ ዓለም አቀፍ ተቋማት ሃላፊዎች ጋር ነው፡፡ የመጽሔቱ ስርጭት ብዙ ባይሆንም በሞስኮ፣ በኬፕታውንና በሻንጋይ ከተሞች ለገበያ ይቀርባል፡፡ ከተመሠረተ 4 ዓመት ሆኖታል፡፡ እኔ በፕሬዚዳንትነት እየመራሁት ነው። በዓለም ዙሪያ እየከፈልናቸው የሚሰሩልን ከ200 በላይ ጋዜጠኞች አሉን፡፡ በራሽያ፣ በቻይና እና በተለያዩ የአፍሪካ አገራት ለሚገኙ ኩባንያዎች የኢኮኖሚ ትንታኔዎችን እንሠራለን፡፡
በኢትዮጵያ እየተሰሩ ስላሉት የመሠረተ ልማት ግንባታዎች ምን ይላሉ?
ኢትዮጵያ በዓለም በፈጣን የኢኮኖሚ ዕድገት ላይ ከሚገኙ አገራት አንዷ መሆኗ እውነት ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ስትመለከተው ግዙፍ የመሠረተ ልማት እንቅስቃሴዎች መኖራቸው ተገቢ ነው፡፡ በቂ ነው ለማለት ግን አልደፍርም፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት እኮ ከፍተኛ ነው፡፡ እስከ 100 ሚሊዮን መድረሱ አይቀርም፡፡ ከዚህ የህዝብ ብዛት አንጻር በብዙ ነገሮች ገና ነን፡፡ በቂ አይደሉም፡፡
የህይወት ፍልስፍናዎ ምንድነው?
ትልቁ ነገር ደግነት ነው፡፡ የተቸገረውን መርዳት፣ የወደቀውን ማንሳት፣ የሞተውን መቅበር። በህይወት እስካለህ ድረስ ደግ መስራት ጥሩ ነው፡፡ እውቀት ያለው እውቀቱን፣ ገንዘብ ያለው ገንዘቡን፣ ጉልበት ያለው ጉልበቱን ለሌላው ማካፈል አለበት። ኢትዮጵያ ከዓለም ሁሉ የምትለየው በዚህ ነው፡፡
ወደ አገር ቤት የመመለስ ሃሳብ አለዎት?
ከአገር ቤት ከጠፋሁ 5 ዓመት ሆኖኛል፡፡ ጊዜ አልነበረኝም፡፡ በተለያዩ የራሽያ ጐረቤት አገሮች ብዙ ስራዎች ነበሩኝ፡፡ በሞስኮ ስኖር ከአገሬ ውጭ እንደሆንኩ አልቆጥረውም፡፡ ሁልጊዜ ከአገር ቤት እንግዶች ይመጣሉ፡፡ ከኤምባሲው ጋር የኢትዮጵያን ጉዳዮች አብረን ነው የምንሰራው፡፡ ለ12 ዓመታት በሞስኮ የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ፕሬዝዳንት በመሆን አገለግያለሁ፡፡ አሁን ደግሞ በሞስኮ ውስጥ የአፍሪካ ማህበረሰብ እየሰራሁ ነው፡፡

         እዚሁ አዲስ አድማስ፣ አንድ ፀሐፊ “ዘመኑ የሴቶች ሆኗል” በማለት አስተያየቱን እንዳካፈለን ትዝ ይለኛል። አመት ሳይሞላው አይቀርም። ያኔ በለንደን ኦሎምፒክ ማግስት መሆኑ ነው። በኦሎምፒክ ውድድሩ ከተካፈሉት ኢትዮጵያዊያን አትሌቶች መካከል፣ የወርቅ ሜዳሊያ በማጥለቅ የታሪክ መዝገብ ውስጥ የሚሰፍር ታላቅ ጀብድ የሠሩት ሦስት አትሌቶች አይደሉ? ሶስቱም ጀግኖች፣ ወጣት ሴት አትሌቶች ናቸው - ጥሩነሽ ዲባባ፣ መሠረት ደፋርና ቲኪ ገላና።
የአዲስ አድማሱ ፀሐፊ ይህንን የሴት አትሌቶች አስደናቂ ገድል ሲያይ ነው፣ ዘመኑ የሴቶች እየሆነ ነው ብሎ የፃፈው። በከፍተኛ ትምህርት፣ በዘመናዊ የሙያ መስኮች፣ በቢዝነስ ሥራም እንዲሁ፣ ሴቶች በየቦታው ብቅ ብቅ ማለት ብቻ ሳይሆን ጎላ ጎላ እያሉ መምጣታቸውንም ታዝቧል። ይሄውና ዘንድሮም፣ ያንን ሃሳብ የሚያጠናክር እንጂ የሚያስቀይር ነገር የተፈጠረ አይመስልም።
በእርግጥ፣ በሞስኮው የአለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ወንድ አትሌቶችም ጥሩ ውጤት አምጥተዋል። ወንድ አትሌቶች አንድ ወርቅ፣ ሶስት ብር እና አንድ ነሐስ አምጥተዋል። ሴት አትሌቶች ደግሞ ሁለት ወርቅና ሶስት ነሐስ። ተቀራራቢ ውጤት ነው። ብሄራዊ ቡድኑም በጥቅሉ፣ በሞስኮ ቆይታው ሶስት የወርቅ ሶስት የብር እና አራት የነሃስ በድምሩ አስር ሜዳልያዎችን በማግኘት ከአለም 6ኛ ከአፍሪካ 2ኛ በመሆን ሻምፒዮናውን አጠናቋል።
በአዲሱ አመት ዋዜማ በሞሪሽየስ በተካሄደው የአፍሪካ ወጣቶች አትሌቲክስ ሻምፒዮና ላይ ግን፣ ሴት አትሌቶች የሚቀመሱ አልሆኑም። ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ከተጎናፀፏቸው 7 የወርቅ ሜዳሊያዎች መካከል፣ 6ቱ በሴት አትሌቶች የተገኙ ናቸው። ይህም ብቻ አይደለም። በውድድሩ ከተገኙት ሰባት የብር እና ስምንት የነሐስ ሜዳሊያዎች መካከል አብዛኞቹ፣ በሴት አትሌቶች ውጤት ናቸው። ለዚያውም፣ ካሁን በፊት በኢትዮጵያውያን አትሌቶች ዘንድ እምብዛም ባልተለመዱት፣ በመቶ ሜትርና በሁለት መቶ ሜትር የሩጫ ውድድሮች የተካፈለች አትሌት፣ ሁለት የብር ሜዳሊያዎችን አጥልቃለች። በአራት መቶ ሜትር የመሰናክል ሩጫ የብር ሜዳሊያ፣ በሌላ የአራት መቶ ሜትር ውድድር ደግሞ የነሐስ ሜዳሊ አግኝተዋል - ኢትዮጵያውያን ወጣት ሴት አትሌቶች። ከ1500 ሜትር በላይ ባሉት ሩጫዎችማ፣ ወርቅ በወርቅ ሆነዋል።
ይሄን ይሄን ስናይ፣ እውነትም ዘመኑ የሴቶች ነው ያሰኛል።

አንዳንዴ ግን ጉዳዮች ሰፋ፣ ነገሮችን ራቅ አድርጎ መቃኘት ያስፈልጋል። ለዚህም ነው፤ ወደ ኋላ መለስ ብዬ የሃምሳ እና የአርባ አመታት የኢትዮጵያ አትሌቶች አለማቀፍ ውጤቶችን ለማነፃፀር የሞከርኩት።
እናስ ምን ተገኘ በሉኝ። ትክክል ነው። የሴት አትሌቶች ውጤት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረና እየገነነ መጥቷል። እስከ 1984 ዓ.ም፣ በኦሎምፒክ አደባባይ ድል ለመጎናፀፍ የቻሉ ኢትዮጵያውያን አትሌቶች በሙሉ ወንዶች ናቸው - አምስት ወንድ አትሌቶች። ምሩፅ ይፍጠር፣ ሁለት ወርቅና አንድ ነሐስ፤ አበበ በቂላ ሁለት ወርቅ፣ ማሞ ወልዴ ደግሞ አንድ ወርቅ፣ አንድ ብር እና አንድ ነሐስ ተቀዳጅተዋል። መሀመድ ከድርና እሸቱ ቱራ ደግሞ ነሐስ።
በ1984ቱ የባርሲሎና ኦሎምፒክ ግን፣ የአበበ በቂላ ታሪክ በሴቶች ተደገመ። ደራርቱ ቱሉ፣ የወርቅ ሜዳሊያ በማጥለቅ የመጀመሪያዋ ኢትዮጵያዊ ሴት የኦሎምፒክ ጀግና ለመሆን በቃች። ከአራት አመታት በኋላ ደግሞ፣ የፋጡማ ሮባ ወርቅ እና የጌጤ ዋሚ ነሐስ ተጨመረበት። በሲዲኒው ኦሊምፒክ ደራርቱ ቱሉ የወርቅ ሜዳሊያ ስትደግም፣ ጌጤ ዋሚ የብርና የነሐስ ባለቤት ሆነች። ከዚያ በኋላማ የሚያቆማቸው አልተገኘም። በጥቂት አመታት ውስጥ የሴቶቹ ድል ከወንዶቹ አትሌቶች ጋር ተቀራራቢ ለመሆን ከመቻሉም በላይ፣ ብልጫ ወደ ማሳየት ተሸጋገረ።
በአለም የአትሌቲክስ ሻምፒዮናም ላይ፣ የሴት አትሌቶች ውጤት በአስገራሚ ፍጥነት ተመንጥቋል።
እንዲያም ሆኖ፤ የወንዶቹ ውጤት እዚያው በነበረት አልቀረም። ከሞላ ጎደል ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻለ መጥቷል። በየጊዜው ከፍ ዝቅ ማለቱ ባይቀርም፣ በጥቅሉ ሲታይ፣ የኢትዮጵያውያን አትሌቶች ውጤት ባለፉት 30 እና 40 አመታት አድጓል፤ ተመንድጓል። የሴት አትሌቶች የስኬት ፍጥነት ግን አጃኢብ ያሰኛል።
በእርግጥ፣ የሴቶች እንቅስቃሴ በጨመረ ቁጥር፣ መንፈስን የሚያነቃቁ የጀብዱና የስኬት ታሪኮች የመበራከታቸው ያህል፣ በተወሰነ ደረጃ አስደሳች ያልሆኑ ቀሽም ታሪኮች መፈጠራቸውም አልቀረም። የትንቢት መልክተኛዋ ጀማነሽንና “የቢግብራዘርዋ” ቤቲን መጥቀስ ይቻላል። ደግነቱ፣ ወደፊት ሳይረሳ የሚቀጥለው ዘመን የማይሽረው ታሪክ፤ የነጥሩነሽ ዲባባና የነመሰረት ደፋር ታሪክ ነው።

  • የፕሬዚዳንቱ ስልጣን፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩን፣ ፓርላማውን፣ እንዲሁም የፌደሬሽን ምክርቤትን ሁሉ ይነካል።
  • ፕሬዚዳንቱ ሳይፈቅድ፣ ጠ/ሚሩ ከፍተኛ ወታደራዊ ማዕረጎችን መስጠትና አምባሳደሮችን መሾም አይችልም።
  • ብዙዎች ቢያናንቁትም የፕሬዚዳንቱ ስልጣን ቀላል አይደለም። “ስልጣኑ ተሠርቶበታል ወይ?” ነው ጥያቄው።

ኢህአዴግ በተለመደው የምስጢራዊነት ባሕርይው፣ ለፕሬዚዳንትነት ማንን በእጩነት እንደሚያቀርብ ሳይነግረን ይሄውና የምርጫው ቀን ደረሰ። ባዕድ መሰልነው እንዴ የሚደብቀን? ዜችን ከመናቅ ይሁን ከመፍራት፣ ሕግን ባለማክበር ይሁን በቸልተኝነት… ምንም ሆነ ምን፣ ዜጎች በሰኞው የፕሬዚዳንት ምርጫና በእጩዎች ላይ ሃሳባቸውን እንዳያቀርቡና እንዳይወያዩ እድል ተነፍጓቸዋል - በኢህአዴግና በፓርላማው። ታዲያ የዜጎች ድርሻ ምንድነው? … ያው እንደተለመደው፣ “ተመልካች” መሆን ብቻ! በቃ፤ ሰኞ እለት ቴሌቪዥን ከፍተው፣ አንድ ሰው ፕሬዚዳንት ሆኖ ሲሾም መመልከት ብቻ! ለነገሩ፣ የአገራችን ችግር የገዢው ፓርቲ ብቻ አይደለም። ብዙዎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ያው ናቸው። አንዳንዶቹም የባሱ! “ለፕሬዚዳንትነት በእጩነት የሚቀርበው ሰው ማን እንደሆነ ለዜጎች ተገልጾ ውይይት መካሄድ አለበት” ብሎ የኢህአዴግንና የፓርላማውን ድብቅነት የተቸ አንድም የተቃዋሚ ፓርቲና ፖለቲከኛ የለም። 
ኢህአዴግ ከዜጎች ጋር በአደባባይ ከመወያየት ይልቅ የጓዳ ምስጢራዊነትን፣ ፓርላማውም በግልፅነት ዜጎችን ከማገልገል ይልቅ የጓሮ ድብቅነትን መምረጣቸው ሳያንስ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች እንዲህ መሆናቸው አይገርምም? ድብቅነትን በመተቸት ግልፅነት እንዲሰፍንና የዜጎች የሃሳብ ነፃነት እንዲሰፍን ሲጠይቁ የማናያቸው፣ ኢህአዴግን ወይም መንግስትን በመፍራት አይደለም። በፕሬዚዳንቱ ምርጫ ዙሪያብዙ ትችቶችን ለመደርደር አልሰነፉም - በተለይ ደግሞ የፕሬዚዳንቱን ስልጣን በማናናቅ።
በአላዋቂነት ይሁን በደንታቢስነት… ምክንያቱ ባይታወቅም፣ የፕሬዚዳንቱን ስልጣን ማጣጣል በኛ አገር በጣም የተለመደ ነገር ነው። ለነገሩ፣ በአገራችን ኋላ ቀር ባህል ውስጥ፣ የመንግስት ስልጣን… “ሕግ የማያግደው አድራጊ ፈጣሪና ፈላጭ ቆራጭ” ካልሆነ፤ ብዙዎቻችን ያን ያህል አናከብረውም፤ እውነተኛ ስልጣን ሆኖ አይታየንም። ለዚህ ይመስለኛል፣ የፕሬዚዳንቱን ስልጣን ማናናቅ እንደ አዋቂነት የሚቆጠረው - በሕግ የተገደበ ስልጣን ስለሆነ!

የኢህአዴግ የድብቅነት ባህል
ኢህአዴግና አጋሮቹ በ99.5% በላይ የተቆጣጠሩት ፓርላማ፣ ባለፈው ሰኔ ወር ላይ የሚኒስትሮች ሹም ሽርና ሽግሽግ እንዴት እንደተካሄደ ታስታውሱ ይሆናል። ባታስታውሱትም ችግር የለውም። እንደተለመደው ነው… አንድ የፓርላማ ስብሰባ ላይ፣ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር መጥተው፣ ለሹመት የታጩ ሰዎችን በስም ይዘረዝራሉ። “እገሌ፣ ይህንንና ያንን ተምሯል፤ እዚህና እዚያ ሰርቷል” የሚል፣ “የአጭር አጭር የመተዋወቂያ ገለፃ ይነበባል - ከሦስት ዓረፍተ ነገር ያልበለጠ። ከዚያ አንድ ሁለት ጥቅል አስተያየቶች በአጭሩ ይቀርቡና የፓርላማ አባላት ድምፅ ይሰጣሉ። የሚኒስትሮቹ ሹመት ይፀድቃል። እስከዚያች የስብሰባ ሰዓት ድረስ፣ ለሚኒስትርነት የታጩት ሰዎች እነማን እንደሆኑ አይታወቅም፤ በምስጢር ተደብቆ ይቆያል። የፓርላማ አባላት እንኳ፣ “ማን በእጩነት ይቀርባል?” ተብለው ቢጠየቁ፣ ከስብሰባው በፊት እንደማያውቁ ነው የሚናገሩት።
ለሚኒስትሮች ሹመት የሚሰጠው አቅምና ብቃታቸው እየታየ መሆን እንዳለበት ሕገመንግስቱ በግልፅ ይደነግጋል። የእጩ ተሿሚዎችን አቅምና ብቃት የመመዘን ስልጣንና ሃላፊነት የፓርላማው የመሆኑን ያህል፤ በእጩዎቹ አቅምና ብቃት ላይ መረጃ መስጠትና ሃሳብ መግለፅ ደግሞ የእያንዳንዱ ዜጋ ነፃነትና መብት ነው። መንግስት፣ የግልፅነት አሰራርን በመከተል እቅዶቹን በይፋ የማስታወቅ ግዴታ በህግ የተጣለበት በሌላ ምክንያት አይደለም። በእቅዶቹ ላይ ዜጎች ሃሳባቸውን የመግለፅና የመወያየት ነፃነት ስላላቸው ነው። “መንግስት እና ፓርላማው የህግ የበላይነትን በማክበር ሃላፊነታቸውን ለማሟላት፣ የዜጎችንም መብትና ነፃነት ለማክበር ፈቃደኛ ቢሆኑ”… ብለን እናስብ። ያን ያህልም ውስብስብ አይደለም።
ለሚኒስትርነት ወይም ለፕሬዚዳንትነት የሚታጩ ሰዎች እነማን እንደሆኑ፣ ከሳምንታት አስቀድሞ የፓርላማ አባላት እንዲያውቁት ይደረግና፣ ለዜጎችም በይፋ ይገለፃል። ያኔ፣ የእጩዎቹን ማንነት በማጥናትና መረጃ በመሰብሰብ፣ ብቃታቸውንና የስነምግባር ደረጃቸውን የመመዘን እድል ይፈጠራል። ዜጎችና የፓርላማ አባላት፣ ሃሳብ ለመለዋወጥና ለመወያየት ጊዜ ያገኛሉ። በእጩዎቹ ብቃትና ድክመት ወይም የስነምግባር ፅናትና ብልሹነት ላይ፣ የሚያስመሰግን ወይም የሚያስወቅስ ተጨባጭ መረጃ ያላቸው ሰዎች፣ ማስረጃቸውን ለፓርላማ አባላት በማካፈል ይተባበራሉ - ሃሳባቸውን የመግለፅ ነፃነታቸውን በመጠቀም። እንዲህ፣ በስልጣኔ ደህና የተራመዱ አገራት ውስጥ እንደሚደረገው፣ ግልፅነትና ጨዋነትን የተላበሰ፣ የህግ የበላይነትና የዜጎች ነፃነትን ያከበረ አሰራር ቢፈጠር፣ በሙስናና በብቃት ጉድለት የሚፈጠሩ ግርግሮች በቀነሱ ነበር። ይሄ ግን አልሆነም።
መንግስት በህግ የተጣለበትን የግልፅነት አሰራርን ወደ ጎን ብሎ፣ ለፕሬዚዳንትም ሆነ ለሚኒስትር ሹመት በእጩነት የሚያቀርባቸውን ሰዎች በምስጢር ደብቆ ይይዛል። የተሿሚዎችን ብቃትና ስነምግባር ፈትሸው እየመመዘን ህገመንግስታዊ ሃላፊነት የተጣለባቸው የፓርላማ አባላትም፣ ሃላፊነታቸውን መወጣት ያቅታቸዋል። በአንድ ስብሰባ ላይ የእጩ ሚኒስትሮች ወይም የእጩ ፕሬዚዳንት ስም ዝርዝር የሚቀርብላቸው የፓርላማ አባላት፤ እዚያው ስብሰባ ላይ የእጩዎችን የቀድሞ የሥራ ትጋትና ስንፍና፣ ስኬትና ውድቀት መርምረው፣ የወደፊት አላማቸውንና ሃሳባቸውን ፈትሸው፣ ብቃትና አቅማቸውንም ሁሉ በአምስት ደቂቃ ውስጥ መዝነው፣ በአምስት ደቂቃ ውስጥ የሁሉንም ሹመት ማፅደቅ የሚችሉት እንዴት ነው? አንድ ሾፌር፣ አንድ ነርስ ወይም አንድ የመዝገብ ቤት ሰራተኛ ለመቅጠር እንኳ ከዚህ የበለጠ ጊዜ ያስፈልጋል። የብቃትና የስነምግባር ጉዳዮችን ለመመርመርና ለመመዘን ይቅርና፣ የሚኒስትሮችን ስም በወጉ ለማወቅ እንኳ በቂ ጊዜ አያገኙም። በብልሹ ምግባር ከስልጣን የሚባረሩ ባለሥልጣናትን፣ በብቃት ጉድለት ሳቢያ የሚሰናበቱ ተሿሚዎችን በየጊዜው የምናየው፣ ከመነሻው ያለበቂ ፍተሻና ምዘና ሹመት ስለሚሰጥ ሊሆን ይችላል።
መንግስትስ የዜጎችን ሃሳቦች ለማሰባሰብና ለመወያየት መሞከር የለበትም? የፓርላማ ተመራጮች፣ በየቀበሌውና በየወረዳው ከመራጮች ጋር መወያየት የለባቸውም? ፓርቲዎችና ፖለቲከኞችስ?
ለዚህ የውስጥ ለውስጥ አሰራር መነሻ ሊሆኑ የሚችሉ ሦስት ምክንያቶች ይታዩኛል። አንደኛው ምክንያት፣ ሕጉ ምንም ይበል ምን፣ እስከ ዛሬ በተለመደው አሰራር በደመነፍስ የመጓዝ ልማድ ነው። ለመንግስት መሪዎችና ለፓርላማ አባላት፣ ለፓርቲዎችና ለፖለቲከኞች፣ ለምሁራንና ለዜጎች ሁሉ… ያን ያህልም ስህተት ሆኖ አይሰማቸውም። ድብቅነት፣ በአገራችን ፖለቲካ ውስጥ ለዘመናት የቆየ ባህልና የተለመደ አሰራር ነዋ። የጎጂ ልማድና የመጥፎ አመል ጉዳይ ነው።
ሁለተኛ፤ መንግስትን እንደ ቁጡ አባት፣ ዜጎችን እንደ ደካማ ሕፃን አድርገን የምናስብ መሆናችን ነው። እንዲህ መንግስትን እንደ ቁጡ አባት ወይም እንደ ጣኦት የማምለክ ኋላቀር ባህልና አስተሳሰብ ስለተጠናወተን፣ መንግስት ምንም ነገር ቢያደርግ፣ የዜጎችን ነፃነት ቢያፍን እንኳ፣ “መልካም ነገር አስቦ ይሆናል” እንላለን። ቁጡ አባት ምንም ቢያደርግ፣ “ለልጆቹ መልካም ነገር አስቦ ይሆናል” እንደምንለው አይነት ነው። ቁጡ አባት ምንም ነገር ሲያቅድ፣ ወደ ውሳኔ ከመሄዱ በፊት እቅዶቹን ለልጆቹ ማማከርና ሃሳባቸውን እንዲገልፁ የማድረግ ግዴታ አለበት? እሺ፣ ቢያማክራቸውና ሃሳባቸውን እንዲገልፁ ቢፈቅድላቸው ጥሩ ነው እንበል። ግን፣ ይህንን ባያደርግ እንደ ወንጀል ወይም እንደ ክፋት አንቆጥርበትም። “ዞሮ ዞሮ ለልጆቹ መልካም ነገር ማሰቡ አይቀርም። ለልጆቹ ምን እንደሚበጃቸው እሱ ያውቃል” እንላለን። እንደ ቁጡ አባት የምንቆጥረው መንግስትም፣ እቅዱን ባያሳውቀን፣ ዜጎችም ሃሳባቸውን እንዲገልፁ ባይፈቅድ፣ ህገመንግስቱን እየጣሰ ቢሆንም እንኳ ትልቅ ጥፋትና ወንጀል ሆኖ አይታየንም። መንግስትን እንደ ቁጡ አባት የመቁጠርና፣ “የሚበጀንን እሱ ያውቅልናል” የሚል ኋላቀር አስተሳሰብ አልለቀቀንማ።
ሦስተኛ፣ የመንግስት ባለስልጣናት እቅዳቸውን በማሳወቅ ከዜጎች አስተያየት ከጠየቁ፣ አላዋቂና ደካማ የሆኑ ይመስላቸዋል። እኛም፣ አላዋቂና ደካማ እንደሆኑ በመቁጠር፣ ከፍ ዝቅ እናደርጋቸዋለን። እንፈታተናቸዋለን። እነሱ ህጋዊውን መንገድ ጥሰው ያሰኛቸውን ነገር ከመፈፀም ይልቅ ዜጎችን ለማማከር ከሞከሩ፤ በእነሱ ፋንታ አዛዥ ናዛዥ ለመሆንና ዙፋን ላይ ቂብ ለማለት ይቃጣናል። እዚያ ድረስ ባንሄድ እንኳ፣ በንቀት መረን ለቀን፣ ጨዋነትን ጥሰን መሳደብ፣ ማንጓጠጥ፣ ሥም ማጉደፍ ያምረናል። ስድቡና ዘለፋው እየተግለበለበ ወደ ውግዘትና ውንጀላ ይሸጋገርና ምስቅልቅል ይፈጠራል። የማዘዝና የመታዘዝ፣ የመርገጥና የመረገጥ ባህል እንጂ፣ ተከባብሮ የመነጋገር ባህል የለማ። እናስ፣ መንግስትና ባለስልጣት ምን ያደርጋሉ? ስልጡን ባህል ለመፍጠር ከመጣጣር ይልቅ፣ አቋራጩን መንገድ ይመርጣሉ - በምስጢር ደብቆ ማቆየትና የእጩ ፕሬዚዳንቱን ወይም የእጩ ሚኒስትሮችን ስም በመዘርዘር በአምስት ደቂቃ ውስጥ ሹመታቸው እንዲፀድቅ ማድረግ! ይሄ ስንፍና ነው። መንግስት፣ በስልጣኔ እንደተራመዱት አገራት ባይሆን እንኳ፣ የእጩ ተሿሚዎችን ስም ከሁለት ከሦስት ቀን በፊት በማሳወቅ፣ የለውጥ ጅምር ማሳየት ይችላል። ለከርሞ ደግሞ የእጩ ተሿሚዎቹን ከሳምንት በፊት በይፋ ማሳወቅ… ቀስ በቀስ ስልጡን የግልፅነት አሰራርን መጀመር ይችላል። ከመርገጥና መረገጥ አባዜ የመላቀቅ ፍላጎት ካለው ማለቴ ነው።

የተቃዋሚዎች ዝርክርክነት
ከላይ እንደገለፅኩት፣ መንግስት በድብቅነት አባዜው፣ የዜጎች ሃሳብን የመግለፅ ነፃነት መጣሱ ሳያንስ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የመንግስትን ድብቅነት በዝምታ በማለፍ የፕሬዚዳንቱን ስልጣን ለማናናቅ መረባረባቸው ያሳዝናል። ፕ/ር መስፍን ወልደማሪያም የሰጡትን አስተያየት ልጥቀስላችሁ።
“የፕሬዚዳንቱ ስራ ዝም ብሎ ቁጭ ማለት ነው፡፡ ወደ 12 ዓመት ገደማ ቁጭ ብሏል፤ ይወጣል፤ በቃ አለቀ፡፡ … ህጉ ራሱ ምንም ሀላፊነት እና ሥራ አይሰጠውም፡፡ በህጉ ላይ የተወሰኑ ነገሮች አሉ፡፡ ሰዎችን መቀበል፣ እንግዶችን ማስተናገድ፣ አምባሳደሮችን መቀበልና መሸኘት፣ ይቅርታ መስጠት… የመሳሰሉትን ያከናውናል”
የፕ/ር መስፍን አስተያየት በጣም አስገራሚ ነው። አንደኛ ነገር፣ በህገመንግስቱ ላይ የሰፈሩት የፕሬዚዳንቱ ዋና ዋና ሥራዎች፣ በፕ/ር መስፍን የተጠቀሱት ነገሮች አይደሉም። ሁለተኛ ነገር፣ የፕሬዚዳንቱ ስልጣን የውጭ አገራት አምባሳደሮችን መቀበልና መሸኘት እንዲሁም ለእስረኞች ይቅርታ መስጠት ቢሆን እንኳ፣ ትንሽ ስልጣን አይደለም። በሁለት አገራት ግንኙነት ውስጥ፣ ከውጭ የተላከ አምባሳደርን ወዲያወኑ አስተናግዶ የሹመት ደብዳቤውን በመቀበል ወዲያውኑ ሥራውን እንዲጀምር ማድረግ፣ ትልቅ የወዳጅነት ምልክት ተደርጎ ይቆጠራል። ፕሬዚዳንቱ ከአሜሪካ ወይም ከአውሮፓ የመጣውን አምባሳደር ባያስተናግዱትና ለረዥም ጊዜ የሹመት ደብዳቤውን ሳይቀበሉ ቢያጉላሉትስ? ይሄም የቅሬታና የጠላትነት ስሜት የሚገለፅበት የዲፕሎማሲ መሳሪያ እንደሆነ ይታሰባል። ፕሬዚዳንቱ ይህንን የመጠቀም ስልጣን አላቸው። የፕሬዚዳንቱ ዋና ዋና ስልጣኖች ግን፣ ከዚህም በእግጁ የገዘፉ ናቸው።
ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣኖች መካከል ሁለቱን ልጥቀስ - የውጭ አገር ግንኙነት እና የመከላከያ ሃይል ፖሊሲዎችን መምራት! በእነዚህ ቁልፍ ስልጣኖች ውስጥ፣ ፕሬዚዳንቱም የማይናቅ ድርሻ አላቸው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ተለያዩ አገራት አምባሳደሮችን ሳይልክ የውጭ ግንኙነቶችን መምራት አይችልም። ለከፍተኛ የጦር መኮንኖች የማዕረግ ሹመት ሳይሰጥም፣ የመከላከያ ሃይል ፖሊሲውን ተግባራዊ ማድረግ አይችልም። ነገር ግን፣ ያለ ፕሬዚዳንቱ ይሁንታ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አምባሳደሮችን መሾም ወይም ለጦር መኮንኖች ከፍተኛ ማዕረግ መስጠት አይችልም። ፕሬዚዳንቱ የእጩ አምባሳደሮችን ሹመት ወይም የጦር መኮንኖቹን የማዕረግ እድገት፣ የማፅደቅ ወይም ውድቅ የማድረግ ስልጣን አላቸው። ይሄ ቀላል ስልጣን ነው? በውጭ ጉዳይ እና በመከላከያ ሃይል ፖሊሲዎች ላይ ተሰሚነትና ተፅእኖ እንዲኖረው የሚያደርግ ከፍተኛ ስልጣን ነው።
በእርግጥ፣ የእስካሁኖቹ ፕሬዚዳንቶች፣ ይህንን ከፍተኛ ስልጣን በአግባቡ አልሰሩበትም ይባል ይሆናል። ይሄ ግን ሌላ ጥያቄ ነው። በጣም ሰፊ ስልጣን በህገመንግስት የተሰጠው ፓርላማስ፣ ስልጣኑን በአግባቡ ሰርቶበታል እንዴ? ግን ስልጣኑ አለው፤ ሊሰራበትም ይችላል። ፓርላማው ካለፈው አመት ወዲህ፣ ሚኒስትሮችን የመቆጣጠር ስልጣኑን በመጠቀም ደህና እንቅስቃሴ ሲያደርግ አይተን የለ? ልክ እንደዚያው፣ ፕሬዚዳንቱም፣ እስካሁን በጉልህ ተግባራዊ ሲደረጉ ያልታዩትን ስልጣኖች ስራ ላይ ማዋል ይችላል። የሆነ ሆኖ፣ የፕሬዚዳንቱ ስልጣን፣ ፕ/ር መስፍን እንዳሉት እንግዶችን መቀበልና በመሳሰሉ መለስተኛ ሃላፊነቶች የታጠረ አይደለም።
ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም፣ ስለ ፕሬዚዳንቱ የስልጣን ቦታና ስለ ሥራ ሃላፊነቱ ወደሰጡት አስተያየት ልሻገር። “ቦታው ለምልክትነት ካልሆነ ብዙ የሚሰራበት አይደለም በሚለውም አልስማማም” የሚሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤ “ፕሬዚዳንቱ ሊያከናውኗቸው የሚችሏቸው የተለያዩ ተግባራት አሉ” በማለት የሰጡት አስተያየት ከፕ/ር መስፍን አስተያየት የተለየ ይመስላል። ግን አይደለም። ዶ/ር ያዕቆብም ቢሆኑ፣ በሕግ የተቀመጠው የፕሬዚዳንቱ ስልጣን፣ እንግዳ ከመቀበልና በአመት አንዴ በፓርላማ ስብሰባ የመክፈቻ ንግግር ከማድረግ የዘለለ እንዳልሆነ ያምናሉ። “በግልፅ የተቀመጡትን እንግዳ መቀበል፣ ፓርላማ መክፈት እና የመሳሰሉትን ትተን፣ በርካታ ስራዎችን መከወን ይችሉ ነበር” ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፣ ፕሬዚዳንቱ የበጐ አድራጐት ስራዎችን መምራት፣ ማህበራትን ማጠናከር፣ ህዝቡን ለስራ ማደፋፈር፣ እስረኞችንና ህሙማንንን እየጎበኙ መከታተልና የመሳሰሉትን ሊሰሩ ይችሉ ነበር ብለዋል።
የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ሙሼ ሰሙ የሰጡት አስተያየትም ተመሳሳይ ነው። “ፕሬዚዳንት ግርማን የማውቃቸው በአገር ምልክትነታቸውና መገለጫነታቸው ብቻ ነው” ያሉት አቶሙሼ ሰሙ፣ “ፕሬዚዳንቱ ህገመንግስቱ ሰፍሮ ከሰጣቸው ስልጣን ባለፈ ሊሰሯቸው የሚችሏቸው ሥራዎች ሞልተዋል፡፡ ለምሳሌ የፕሬዚዳንቱ ቦታ የዲፕሎማቲክ ስራዎችን እንዲሰሩ ያደርጋቸዋል፡፡ ብዙ ማህበራዊ እንቅስቃሴዎችም አሉ” ብለዋል። የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ዘለቀ፣ የፕሬዚዳንቱ ቦታ እዚህ ግባ የሚባል ስልጣን በህገመንግስቱ እንዳልተሰጠውና የፖለቲካ ቁምነገር የሌለው ቦታ እንደሆነ ጠቅሰው፣ ህገመንግስቱ ላይ ባይቀመጥም ፕሬዚዳንቱ ብዙ ሊሰሯቸው የሚገቡ በጎና ማህበራዊ ነገሮች መኖራቸውን ገልፀዋል።
የአገላለፅ ልዩነት ቢኖራቸውም፣ ዶ/ር መስፍን፣ ዶ/ር ያዕቆብ፣ ኦቶ ሙሼ እና አቶ ዘለቀ የሰነዘሯቸው አስተያየቶች፣ ፕሬዚዳንቱ እንግዳ ከመቀበልና ከመሸኘት ያለፈ ስልጣን በህገመንግስት አልተሰጣቸውም፤ ነገር ግን ፖለቲካዊ ያልሆኑ ስራዎችን ማከናወን ይችላሉ የሚል ሃሳብ ያዘሉ ናቸው።
በእርግጥም፣ ፕሬዚዳንቱ በአገሪቱ ውስጥ ያላቸውን ተሰሚነት በመጠቀም በርካታ በጎ ነገሮችን ማበረታታት ይችላሉ። ነገር ግን፣ በህገመንግስት የተዘረዘረው የፕሬዚዳንቱ ስልጣን፣ እንግዳ መቀበል፣ አመታዊ የፓርላማ ስብሰባ መክፈትና የመሳሰሉት ብቻ አይደለም። በተለይ ዶ/ር ያዕቆብ፣ የሕግ ባለሙያ እንደመሆናቸው፣ እንዲህ አይነቱን ስህተት መስራታቸው ያስገርማል። ለነገሩ፣ ፕሬዚዳንቱን በማሞገስ አስተያየት የሰጡት የፓርላማ አባል ዶ/ር አሸብር ወልደ ጊዮርጊስ እና የፕሬዚዳንቱ ረዳትና የሕግ ባለሙያው አቶ አሰፋ ከሲቶም፣ ተመሳሳይ የተሳሳተ አስተሳሰብ አስተጋብተዋል።
የፕሬዚዳንቱን ስልጣን ለማናናቅ በተደጋጋሚ የሚጠቀስ አንድ አንቀፅ አለ። በፓርላማ የፀደቀ አዋጅ፣ ስራ ላይ የሚውለው ፕሬዚዳንቱ በፊርማ ሲያሳልፉት እንደሆነ የሚገልፀው የአገሪቱ ሕገመንግስት፣ ፕሬዚዳንቱ ፈቃደኛ ባይሆኑ እንኳ ህጉ ስራ ላይ እንዳይወል ማድረግ የሚችሉት ለ15 ቀን ያህል ብቻ ነው። በእርግጥ፣ አንድን ህግ ወዲያውኑ ስራ ላይ እንዲውል ማድረግ ወይም ለ15 ቀን ማዘግየት፣ ሰፊ ስልጣን አይደለም። እንዲያም ሆኖ፣ በተለይ አጣዳፊና አወዛጋቢ በሆኑ ህጎች ላይ፣ ለምሳሌ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እና የጦርነት አዋጅ በመሳሰሉ ውሳኔዎች ላይ፣ ለ15 ቀናት አዋጁ ታግዶ እንዲቆይ የማድረግ ስልጣን ቀላል ስልጣን አይደለም።
ፕሬዚዳንቱ፣ በፓርላማ የሚወጡ ህጎችም ሆኑ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የሚወጡ ደንቦች ላይ ተጨማሪ ተፅእኖ የማሳረፍ እድል አላቸው። ህጎችና ደንቦች፣ ከህገመንግስት ጋር የሚጋጩ መሆን አለመሆናቸውን በመመርመር የውሳኔ ሃሳብ የማቅረብ ስልጣን በተሰጠው ለህገመንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ እንደሆነ ይታወቃል። 11 አባላትን ባካተተው አጣሪ ጉባኤ ውስጥ፣ የስድስቱ አባላት ሹመት የሚፀድቀው በፕሬዚዳንቱ ይሁንታ ነው። በቀነ ገደብ የታጠረ ስልጣንም አይደለም። በቃ! ፕሬዚዳንቱ ካልተስማሙበት ሹመቱ አይፀድቅም። የአምባሳደሮች ሹመትና የጦር መኮንኖች ማዕረግም፣ ያለ ፕሬዚዳንቱ ይሁንታ ተግባራዊ ሊሆን አይችልም።
ይሄ፣ ቀላል ስልጣን ነው? በጭራሽ አይደለም። ይልቅስ፣ ይሄ የፕሬዚዳንቱ ከፍተኛ ስልጣን በአግባቡ ተግባራዊ ሳይደረግ ቆይቷል ከተባለ፣ አዎ አልተደረገም። ለምሳሌ፣ ፕሬዚዳንቱ የተሿሚ አምባሳደሮችንና ከፍተኛ ማዕረግ የሚሰጣቸው የጦር መኮንኖችን ጉዳይ የሚመረምር፣ መረጃ የሚያሰባስብ የባለሙያዎች ቡድን የላቸው።

“የአሜሪካ መንግስት ተዘጋ፤ የመንግስት መሥሪያ ቤቶች በር ተከረቸመ” የሚለው ሰሞነኛ የውዝግብ ዜና፣ እውነት ቢሆንም የተጋነነ ነገር አለው። አዎ፤ አብዛኞቹ መሥሪያ ቤቶች ተዘግተዋል። ነገር ግን ሁሉም አልተዘጉም። እንደ ኤፍቢአይ የመሳሰሉ የፍትህ አካላት፣ እንደ ሲአይኤ የመሳሰሉ የስለላ ተቋማት በከፊል እንጂ ሙሉ ለሙሉ አልተዘጉም። የመከላከያ ሃይል ተቋማትም ስራቸውን አላቋረጡም። በርካታ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ከሞላ ጎደል ተከርችመዋል። ከዚሁ ጋርም፣ 800 ሺ ገደማ የሚሆኑ የመንግስት ሰራተኞች፣ ደሞዝ የማይከፈልበት እረፍት እንዲወስዱ ተነግሯቸው ስራ ፈትተዋል፤ ወደ ስራ ተጠርተው እስኪመለሱም ድረስ የመተዳደሪያ ገቢ አይኖራቸውም። በእርግጥ “የመንግስት ሠራተኛ ድሮስ መቼ ሠርቶ ያውቃል?” ብለው በቢሮክረሲው ዝርክርክነት የሚያሾፉ ሰዎች ደግሞ፣ “ሳይሰራ ደሞዝ ይከፈለው ነበር፤ አሁን ግን ሳይሰራ ገንዘብ አለማግኘትን ደግሞ ይሞክረው!” ማለታቸው አልቀረም። በእርግጥም፤ የመሥሪያ ቤቶቹ ሰሞኑን የተዘጉበት የውዝግብ መነሻ፤ ከገንዘብ ጋር የተያያዘ ነው - ከመንግስት ወጪና ባጀት ጋር።

ዋናዎቹ አወዛጋቢ ጉዳዮች ሶስት ናቸው፣ ከአመት አመት የሚያብጠው የመንግስት በጀት፣ በጊዜ ወደ ጊዜ የሚቆለለው የመንግስት እዳ እና “ኦባማኬር” የተሰኘው አስገዳጅ የጤና ኢንሹራንስ። ተወዛጋቢዎቹስ እነማን ናቸው? በአንድ ወገን፣ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ እና መቶ መቀመጫዎች ባሉት ሰኔት ውስጥ አብላጫውን ወንበር የተቆጣጠሩ የዲሞክራቲክ ፓርቲ ተመራጮች አሉ። በሌላኛው ወገን ደግሞ፣ 435 መቀመጫዎች ባሉት ኮንግረስ ውስጥ፣ አብላጫውን ወንበር የተቆጣጠሩ የሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች አሉ። በእነዚህ ሁለት ወገኖች መካከል ላለፉት ሶስት አመታት እየተካረረ የመጣው ውዝግብ፣ ሰሞኑን መፈናፈኛ ወዳልተገኘለት አጣብቂኝ ስለተሸጋገረና በበጀት ጉዳይ ላይ ሊስማሙ ባለመቻላቸው ነው የመንግስት መስሪያ ቤቶች የተዘጉት።

ታላቋ የነፃነት አገር አሜሪካ፣ ባለፉት መቶ አመታት ነገረ ስራዋ እየተበላሸ መምጣቱን ከሚመሰክሩ ነገሮች መካከል፣ የሰሞኑ አጣብቂኝ እንደ አንድ ምልክት ሊታይ ይችላል። ውዝግብና አጣብቂኝ መፈጠሩ፣ አልያም የመንግስት መሥሪያ ቤቶች መዘጋታቸውና ሠራተኞች እረፍት እንዲወጡ መደረጋቸው አይደለም ችግሩ። እነዚህ ነገሮችማ፣ አሜሪካ ገና ከሁሉም አገራት የተሻለች የነፃነትና የሕግ አገር መሆኗን የሚጠቁሙ የጤንነት ምልክቶች ናቸው። ይልቅስ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ የመንግስት ወጪ እየተለጠጠና በጀቱ እያበጠ መምጣቱ ነው፣ ትልቁ የበሽታ ምልክት። በጀት ማሳበጥ፣ መዘዞች አሉት። ወጪውን የሚሸፍን በቂ ገንዘብ እንደ ልብ አይገኝማ። እናም መንግስት ወጪውን ለመቀነስ ከመጣጣር ይልቅ፣ በየአመቱ እየገዘፈ የሚመጣውን የበጀት ጉድለት ለመሸፈን፣ በቦንድ ሽያጭ ገንዘብ ይበደራል። ለምሳሌ ባለፉት መንግስት ሶስት አመታት ከ3 ትሪሊዮን ዶላር በላይ ስለተበደረ፣ በድምሩ የመንግስት እዳ ከ16 ትሪሊዮን ዶላር አልፏል።

በእርግጥ፣ የመንግስት ወጪዎችንና በጀቶችን ለመቀነስ መጠነኛ ማሻሻያዎች ተደርገዋል። ከዚህም ጋር የብድር ጣሪያን የሚገድቡ ህጎች በተደጋጋሚ ታውጀዋል። ነገር ግን፣ የብድርና የእዳ አዙሪቱ አልተበጠሰም። እንዲያውም በአዳዲስ ተጨማሪ ወጪዎች፣ ነገሩ ሁሉ እንደ አውሮፓውያኑ የግሪክ እና የስፔን አይነት ተስፋ ቢስነት እንዳያመራ የሚሰጉ አሉ። ለምሳሌ ከውዝግብ ጋር ተገጣጥሞ፣ ማክሰኞ እለት ስራ ላይ የዋለው አስገዳጁ የጤና ኢንሹራንስ ህግ (ኦባማኬር)፣ በየአመቱ በመቶ ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ተጨማሪ ወጪዎችን የሚያስከትል ነው። በዚያው መጠንም የበጀት ጉድለቱና የእዳ ክምሩ ይባባሳል። የዘንድሮውን የበጀት ጉድለት ለመሸፈን ብቻ መንግስት፣ ከ700 ቢሊዮን ዶላር በላይ ተጨማሪ ብድር ያስፈልገዋል።

ነገር ግን፣ ፕሬዚዳንት ኦባማ በገንዘብ ሚኒስትራቸው በኩል ለ“ኦባማኬር” እና ለሌሎች የመንግስት ወጪዎች ያሰኛቸውን ያህል በጀት የመመደብና የበጀት ጉድለቱን ለመሸፈን ያሻቸውን ያህል ገንዘብ የመበደር ስልጣን የላቸውም - ከኮንግረስ ይሁንታ ካላገኙ በስተቀር። የአሜሪካ ውበት ያለው እዚህ ላይ ነው። የመንግስት ስልጣን በሕግ የተገደበ ነው። የመንግስት ወጪ በግማሽ ትሪሊዮን ዶላር ለመቀነስና “ኦባማኬር”ን ለማስወገድ ከመሞከር ያልቦዘኑት ሪፐብሊካኖች በበኩላቸው፣ ህጉን ለመሻር 40 ያህል አዋጆችን አርቅቀው ቢያፀድቁም፣ በፕሬዚዳንቱና በሰኔቱ ተቀባይነት ስላላገኙ ውድቅ ተደርጎባቸዋል። አንዱ የመንግስት አካል፣ ለሌላኛው የመንግስት አካል ልጓም ይሆንለታል። እንግዲህ፤ በአንድ በኩል ኮንግረሱ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ሰኔቱና ፕሬዚዳንቱ ለበርካታ ወራት እንደተፋጠጡ፣ “መስከረም ጠባ”። የዘንድሮው መስከረም እንደሌላው ጊዜ የበጀት ውዝግብን ብቻ አስከትሎ አልመጣም፣ ሌሎች ሁለት ውዝግቦችንም ጨምሮበታል። እንደተለመደው፣ መስከረም 21 ቀን (ኦክቶበር 1 ቀን)፣ አዲስ የበጀት አመት የሚጀመርበት ቀን ስለሆነ፣ የበጀት ውዝግብ መፈጠሩ አይገርምም።

ውዝግቡ መካረሩና በቀላሉ ስምምነት ላይ አለመደረሱ ነው፣ የዘንድሮውን ለየት የሚያደርገው። አዲስ በጀት ካልፀደቀ የመንግስት መስሪያ ቤቶች በራቸውን ይዘጋሉ። አወዛጋቢውና በሪፐብሊካኖች ዘንድ የማይወደደው “ኦባማኬር” የተሰኘው አስገዳጅ የጤና ኢንሹራንስ፣ በይፋ ተግባራዊ መሆን የሚጀምረውም በዚሁ እለት መሆኑ፣ የሁለቱን ወገኖች ውዝግብ አወሳስቦታል። ከሁለት ሳምንት በኋላ (ኦክቶበር 17) ደግሞ፣ የመንግስት የእዳ ክምር በህግ የተቀመጠለትን ጣሪያ ይነካል ተብሎ ይጠበቃል። እናም የብድር ጣሪያ ለመገደብ ከሁለት አመት በፊት የፀደቀው ህግ ካልተከለሰ፣ መንግስት ወጪዎቹን ለመሸፈን ተጨማሪ ብድር ማግኘት አይችልም። የመንግስት አማካይ የሳምንት ወጪ 60 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ቢሆንም፣ አማካይ ገቢው ግን 45 ቢ. ዶላር ገደማ ነው። በየሳምንቱ በአማካይ 15 ቢሊዮን ዶላር ብድር ካላገኘ አመቱን ሊዘልቅ አይችልም። ተንገራግጮ ይቆማል።

እናም፣ በተጨማሪ ብድር አመቱን ለመዝለቅ፣ የእዳ ጣሪያው ከ16.7 ትሪሊዮን ወደ 17.5 ትሪሊዮን ገደማ መስተካከል ይኖርበታል። ግን እስከመቼ እዳ እየተቆለ ይቀጥላል? እንደምታዩት፣ የፍጥጫው አስኳሎች እነዚሁ የበጀት፣ የእዳ እና የ“ኦባማኬር” ውዝግቦች ናቸው ማለት ይቻላል። ፕሬዚዳንት ኦባማ እና አብላጫውን የሰኔት ወንበር የያዙ የዲሞክራቲክ ፓርቲ ተመራጮች፣ የሚያጨቃጭቅ ነገር የለም ባይ ናቸው … “የመንግስት መስሪያ ቤቶች መዘጋት ስለሌለባቸው እንደ አምናው በጀት ሊመደብላቸው ይገባል፤ የበጀት ጉድለቱን ለመሸፈንም የእዳ ጣሪያው መስተካከል አለበት። ይሄ አከራካሪ ሊሆን አይገባውም። ወጪዎችን ለመቀነስ፣ የበጀት ጉድለትን ለማስወገድና የእዳ ክምችትን ለማቃለል፣ መወያየትና መደራደር እንችላለን። ነገር ግን፣ የመንግስት ስራዎች መቋረጥ አይኖርባቸውም” ይላሉ። በኮንግረስ ውስጥ አብላጫውን ወንበር የያዙ የሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች ግን በዚህ አይስማሙም። አምርረው ይቃወሙታል እንጂ። “የመንግስት ወጪ እየተለጠጠ፣ የበጀት ጉድለት እየሰፋና የእዳ ክምችት እየተቆለለ መምጣቱ ሳያንስ፣ ‘በኦባማኬር’ ሳቢያ ችግሩን ይበልጥ የሚያባብስ ግዙፍ ወጪ ሊጨመርበት አይገባም። የእዳ ጣሪያውን በማንሳት ለተጨማሪ ብድር በር ከመክፈታችን በፊት አሁኑኑ የረዥም ጊዜ መፍትሄ ማበጀት ይገባናል። ቢያንስ ቢያንስ፣ ኦባማኬር ሙሉ ለሙሉ ወይም በከፊል ለአንድ አመት ስራ ላይ እንዳይውል ማዘግየት ያስፈልጋል” ይላሉ። በዚህ አቋም ላይ በመመስረት፣ በኮንግረስ የሪፐብሊካኖች መሪ የሆኑት አፈጉባኤ ጆን በይነር ምን አደረጉ? ለአስር ሳምንታት ገደማ የሚያገለግል ጊዜያዊ የበጀት አዋጅ ያዘጋጁትበይነር፣ “ለኦባማኬር ምንም በጀት አይመደብለትም” የሚል ተጎታች ከአዋጁ ጋር በማዳበል የኮንግረስ አባላት ድምፅ እንዲሰጡበት አቀረቡት። አሜሪካ የነፃነት አገር ነውና፣ የፓርቲ መሪዎችን ተከትለው ድምፅ የማይሰጡ የኮንግረስ አባላት መኖራቸው አይገርምም። አብዛኞቹ ሪፐብሊካኖችና 20 ያህል አፈንጋጭ ዲሞክራቶች፣ ባለተጎታቹን የበጀት አዋጅ በመደገፍ ድምፅ ሰጥተዋል።

አብዛኞቹ ዲሞክራቶችና ጥቂት አፈንጋጭ ሪፐብሊካኖች ደግሞ ተቃውመውታል። በድምሩ በ230 ድጋፍ አዋጁ በአብላጫ ድምፅ ፀድቆ ወደ ሰኔት ተላከ። ሰኔቱ ይህንን ባለ ተጎታች የበጀት አዋጅ ቢያፀድቀው፣ ወደ ፕሬዚዳንቱ ነበር የሚሄደው። ነገር ግን፣ እዚያ አልደረሰም። በሴኔት ውስጥ አብላጫውን ወንበር የያዙት ዲሞክራቶች፣ የመጣላቸውን ባለተጎታች አዋጅ ተቀብለው፣ “ለኦባማኬር በጀት አይመደብለትም” የሚለውን አንቀፅ በመሰረዝ ሌጣውን ካስቀሩት በኋላ ሴናተሮች እንዲከራከሩበት አቀረቡት። ድምፅ ይሰጥበት ከተባለ ሌጣው አዋጅ እንደሚፀድቅ አያጠራጥርም - በ54 ዲሞክራት ሴናተሮች ድጋፍና በ46 ሪፐብሊካን ሴናተሮች ተቃውሞ። ነገር ግን፣ ዲሞክራቶች፣ በሰኔት ውስጥ አብዛኛውን ወንበር ስለያዙ ብቻ፣ በቀላሉ አዋጁን ማፅደቅ ይችላሉ ማለት አይደለም። አንድ እንቅፋት ማለፍ አለባቸው - በቅድሚያ የሰኔት ውስጥ የሚደረገውን ክርክር መቋጨት ይኖርባቸዋል።

ምክንያቱም በሰኔት ውስጥ፣ ነገ አራት ሰዓት ላይ ድምፅ ይሰጥበታል ተብሎ የተጀመረው ክርክር፣ በተባለው ሰዓት ላያበቃ ይችላል። ለምን? ሴናተሮች ልዩ መብት አላቸዋ። ተራው ደርሶ መናገር የጀመረ ሴናተር፣ ያለማቋረጥ የቻለውን ያህል ሰዓት ንግግሩን መቀጠል ይችላል። ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ እለት፣ ‘ኦባማኬር’ እንዲወገድ የሚፈልጉ ቴዲ ክሩዝ የተባሉ ሪፐብሊካን ሴናተር፣ ሌጣውን አዋጅ በመቃወም ለ21 ሰዓታት ያለማቋረጥ የሴኔቱን መድረክ ይዘው ነበር። በአዋጁ ላይ ድምፅ ይሰጥበታል የተባለው ሰዓት ካለፈ፣ ማሸጋሸግ ብሎ ነገር የለም። እንደገና እንደ አዲስ የውይይትና የድምፅ አሰጣጥ ፕሮግራም ይወጣል። ነገር ግን አሁንም፣ ያለ ገደብ ለበርካታ ሰዓታት የሚቀጥል አንድ ሴናተር፣ እንደገና የድምፅ አሰጣጥ ፕሮግራሙን በማዛባት ያስተጓጉለዋል።

በዚህ መንገድ፣ አዋጅ እንዳይፀድቅ ማሰናከል፣ ‘ፍሊበስተር’ ተብሎ ይታወቃል። የሴናተር ንግግርና ክርክር ሊቋረጥ የሚችለው፣ 60 ሴናተሮች የሰዓት ገደብ ለመጣል ከተስማሙ ነው። በሌላ አነጋገር፣ በሰኔቱ ውስጥ 54 ወንበር ያላቸው ሴናተሮች፣ ብቻቸውን የውይይት ሰዓት ገደብ እንዲበጅለት መወሰን አይችሉም። ቢሆንም፣ በአሜሪካ ፖለቲካ ውስጥ “በፓርቲ ትዕዛዝ ሰጥ ለጥ ብሎ መመራት” ብሎ ነገር ስለሌለ፣ ዲሞክራቶቹ ከሪፐብሊካን ሴናተሮች መካከል የተወሰነ ድጋፍ ማግኘት ይችላሉ። በመጨረሻም የሪፐብሊካኑ ሴናተር የቴድ ክሩዝ ረዥም ንግግር እንዲያበቃ የሚፈልጉ ሴናተሮች ቁጥር 60 ስለደረሰ፣ ሲናገሩ ውለው ያደሩት ቴዲ ክሩዝ ከ21 ሰዓት ተኩል ገደማ በኋላ ንግግራቸው ለመቋጨት ተገደዋል።

ከዚያማ ሌጣው ሕግ ላይ ድምፅ ተሰጥቶ 54 ለ46 በሆነ ድምፅ ፀደቀና ወደ ኮንግረስ ተመልሶ ተላከ። በኮንግረሱ ውስጥ የሪፐብሊካኖች መሪ ሆነው በአፈጉባኤነት የሚሰሩትበይነር፣ በሰኔት ለከልሶ የመጣውን አዋጅ በኮንግረስ አባላት ድምፅ እንዲሰጥበት አላደረጉም - “ለኦባማኬር በጀት አይመደብለትም” የሚለው ተጎታች ስለተሰረዘ። በዚያ ምትክ ሌላ አዋጅ አርቅቀው አቀረቡ - ለ10 ሳምንታት ገደማ የሚያገለግል ጊዜያዊ በጀትና ኦባማኬር በከፊል ለአንድ አመት እንዲዘገይ የሚደነግግ አዋጅ። አዋጁ ፀድቆ ወደ ሰኔት ሲሄድ ግን፣ ተመሳሳይ እጣ ገጠመው። “ኦባማኬር፣ በከፊል ለአንድ አመት ይዘገያል” የሚለው አንቀፅ ተሰርዞ 54 ለ46 በሆነ ድምፅ ወደ ኮንግረስ ተመለሰ። እንዲህ እንዲህ እያለ፣ በጀት ሳይፀድቅ የበጀት መዝያ እለት ደረሰ - ሰኞ ሴፕተምበር 30። በማግስቱም በጀት አልፀደቀም። ያለበጀት መስራት ስለማይችሉ ለጊዜው እንዲዘጉ የመንግስት መስሪያ ቤቶች መቼ እንደሚከፈቱ አይታወቅም። ለምን? ውዝግቡ መቼ እልባት እንደሚያገኝና መቼ በጀት እንደሚፀድቅ ስለማይታወቅ! ሁለት ሶስት ሳምንት ሊቆይ እንደሚችል ነው የሚገመተው።

(ላታ ኤኬና ሾሮይ ብት ዎሬስ) - የወላይታ ተረት

        ከዕለታት አንድ ቀን፣ ከአንድ እርሻ አጠገብ፣ አንድ ኮሳሳ ውሻ ተኝቶ ፀሐይ እየሞቀ ሳለ፤ አንድ የተራበ ተኩላ ድንገት ከተፍ ይልበታል፡፡ ከዚያም ያንን ውሻ ለመብላት አሰፍስፎ፤ “እንዳትነቃነቅ! የዛሬ ቁርሴ አንተ ነህ!” ይለዋል፡፡ ውሻውም፤ “ጌታ ተኩላ ሆይ! እኔ ባሁኑ ሰዓት ምን ዓይነት ኮሳሳ ፍጥረት እንደሆንኩ ታያለህ! አሁን እኔን በልተህ ምንም አትጠቀምም፡፡ ምክንያቱም አጥንቴ የቀረ ልሞት ጥቂት የቀረኝ እንስሳ ነኝ፡፡” ተኩላም፤ “ታዲያ እንዲሁ ባዶ ሆዴን እንድውልልህ ነው የምትፈልገው?” አለ፡፡ ውሻ፤ “የለም፡፡ ሁለት ሶስት ቀን ብትታገስ፤ የእኔ ጌታ ትልቅ ድግስ ለመደገስ እየተዘጋጀ ነው፡፡ ከድግሱ በርካታ ትርፍራፊ እጄ ይገባል፡፡ ያኔ ብዙውን ሥጋ፤ አጥንትና ቅባት የጠጣ ምግብ፤ ላንተ አስረክብሃለሁ፡፡ ከዛ በኋላ፤ ከፈለግህ እኔን ጨምረህ ለመብላት ትችላለህ” ይለዋል፡፡ ተኩላው፤ በጉጉት ቆበሩን እየደፈቀ፤ “ይሄ በጣም ጥሩ ዕቅድ ነው፡፡

እንዳልከው ትንሽ ቀን መታገስ አያቅተኝም” ብሎ ውሻውን ጥሎ ወደጫካው ሄደ፡፡ በሶስተኛው ቀን ተኩላው ተመልሶ ወደ እርሻው ቦታ መጣ፡፡ ውሻው ግን እበረቱ ጣራ ላይ ተኝቶ ፀሐይ ይሞቃል፡፡ “ደህና ዋልክ አያ ውሻ” አለ ተኩላ፡፡ ውሻም፤ “እንደምን ሰነበትክ፤ ሰሞኑንኮ ከዛሬ ነገ ትመጣለህ እያልኩ ስጠብቅህ ከረምኩ፡፡ ምነው ጠፋህ?” ተኩላም፤ “ሁለት ሦስት ቀን ስላልከኝ፤ ጊዜ ልስጥህ ብዬ ነው፡፡ ይኸው በሶስተኛው ቀን መጣሁ፡፡ ጌታህ ይደግሳል ያልከኝ ድግስ የታለ? በስምምነታችን መሠረት ውረዳ?” ሲል ጠየቀው፤ ምላሱን ካፉ እያወጣ፣ ከንፈሩን እየላሰ የመብላት ስሜቱን በመግለጽ፡፡ ውሻም፤ “አይ አያ ተኩላ! ጌታዬማ ድግሱን ለሚቀጥለው ዓመት አዛወረው፡፡ ከእንግዲህ እኔንም ሁለተኛ ባለፈው ያገኘኸኝ ገላጣ ሜዳ ላይ አታገኘኝም፡፡ በእጅህ የገባልህን ነገር ትተህ፣ ገና ለገና አገኘዋለህ ብለህ፣ በተስፋ የተመኘኸውን ድግስ ልትበላ ስትስገበገብ፤ ሁለት ቀን ፆምህን መዋልህ ነው፡፡ ይልቅ አሁን ጌታዬ መምጫው ስለደረሰ ከዚህ ዞር ብትል ይሻልሃል” አለው፡፡ ተኩላው እየተናደደና እየዛተ መንገዱን ቀጠለ፡፡ ውሻ እየሳቀ ፀሐይ መሞቁን ተያያዘው፡፡

                                                          * * *

ፀሐይ የሚሞቅ ውሻ ሁሉ ሞኝ አይደለም፡፡ ለነገ እበላዋለሁ የሚል ጅል ተኩላ ግን ምን ጊዜም አይጠፋም፡፡ ይህን ሁሉ የሚታዘብ ህዝብ እንዳለ የሚያውቅ ካለ የብልህም ብልህ ነው፡፡ ከላይ ከተረቱም እንደምንረዳው፤ የሌሎችን ግብና አዕምሮ ማማለልንና ማዘናጋትን የሚያውቁበት ሰዎች እንዳሉ አንርሳ! ተስፋ በመስጠት እንደዳማና እንደ ቼዝ ጠጠር (ወታደር) በፈለጉት አቅጣጫ ይገፉናል፡፡ ፍላጐታችንን ያከበሩ በመምሰል ፍላጐታቸውን የሚያሟሉ ሰዎች አደገኞች ናቸው፡፡ የህንዱ ፈላስፋ ካውቲላ “በቀስተኛ የተሰደደ ቀስት፣ አንድን ነጠላ ሰው ሊገድልም ላይገድልም ይችላል፡፡ የተቀመረ ሴራ ግን እናት ሆድ ውስጥ ያለውን ህፃን ሳይቀር ሊገድል ይችላል” ይላል፡፡ በዚህ የተካኑ ሰዎችን በዐይነ - ቁራኛ ማየት ያባት ነው፡፡ ስሜትን ተቆጣጥሮ ደባና ሴራን ጠንቅቆ ማየትና በጠዋት መንቃት ተገቢ ነው፡፡ እንደ ናፖሊዮን “ጠንካራ እጅህን ከሀር በተሰራ ጓንት ውስጥ ክተት” የሚሉ እንዳሉ እንገንዘብ፡፡ ድቀትና ዝቅጠት ሲያይል አሉባልታና ጥርጣሬ ይነግሳል፡፡ አንድም፤ “ጊዜ ሲበሳበስ መሾም መሸለም እየቀለለ ይመጣል”፡፡

(ሄልሙት ክሪስት እንዳለው) በእንዲህ ያለው ሰዓት አፍ - አዊ እየበረከተ፣ ልባዊና ተግባራዊ እየሳሳ ይመጣል፡፡ ይሄኔ መጠንቀቅ ይበጃል፡፡ ኒቼ እንደሚለን “የአንድ ነገር ዋጋ በዚያ ተገልግለን በምናገኘው ጥቅም አይለካም፡፡ ይልቁንም ያንን ነገር ለማግኘት በምንከፍለው መስዋዕትነት ነው የሚለካው”፡፡ አገር እንገነባለን ስንል ይህን ብሂል አለመርሳት ነው፡፡ ይሆነናል የምንለውን ሰው መርጠን ስንሾምም ይህንን አለመዘንጋት ነው፡፡ ባለሙያው እያለ ስለዚያ ሙያ የሚያወራ ሲበዛ ጠንቀቅ ማለት ያሻል፡፡ “አያገባው ገብቶ አያወዛው ተቀብቶ” እንደተባለው መሆኑን ልብ ማለት ነው፡፡ መጪዎቹ የፓርላማ ጊዜያት የጠነከሩ፣ ልባዊነት የሞላባቸውና አመርቂ እንዲሆኑ እንመኝ፡፡ “ሸንጐ/አደባባይ የሰለጠነ ጦርነት ነው” የሚባለው በዋዛ አይደለም፡፡ መሪዎች የሸንጐን ጥበብ መካን አለባቸው፡፡ አደባባይ መዋል የራሱ የክት ጠባይ አለው፡፡ “ሸንጐ የሚያውቅ ሰው፤ መልኩን መቆጣጠር ይችላል፡፡ በቀላሉ ልቡን አይሰጥም፡፡ ለክፉ አድራጊዎች ዕድል አይሰጥም፡፡ ለጠላቶቹ ፈገግ ማለት ይችላል፡፡ ንዴቱን መዋጥ ያቅበታል፡፡ ወገናዊነቱን መሸፈን ይችላል፡፡ የልቡን ደብቆ እሱ በዚያች ቅጽበት ልመስል ወይም ልሆን ይገባኛል የሚለውን፤ የሚፈልገውን ስሜት ያስተናግዳል፡፡ የራሱን ቦታ፣ መሬት፤ አገር፣ ውሉን አይስትም” ይለናል፤ ፈረንሣዊው ዣን ዴላ ብሩዬር፡፡ ፕሬዚዳንት ስንመርጥ እንዲህ ያለውን ቁም ነገር አንርሳ፡፡

ህግ ብቻውን ሁሉን ጉዳይ አይጨርስልንም፡፡ አስተዋይ አመራር፣ አስፈፃሚና ተጠያቂነትን ገምጋሚ እንዲኖር ያሻል፡፡ ያ ደግሞ ግልጽነትን ልማድ የሚያደርግ መሆን አለበት፡፡ አሉባልታ የሚቆመው ግልፅነትና መረጃ ሰጪነት ሲከበር ነው፡፡ “የፕሬዚዳንቱ ቤት ኪራይ ጉዳይ፤ የእገሊት የውጪ ባንክ ገንዘብ ጉዳይ፣ የእነ እገሌ ህንፃ… ይሄ ተሸጠ፣ ያ ተገዛ…ወዘተ” የጥርጣሬና የሟርት ዘመን ምልኪዎች ናቸው፡፡ በምንም ዓይነት ግን የፖለቲካ ትግልን እንደማይተኩልን ማሰብ ተገቢ ነው! የፖለቲካ ትግል ከሁሉም በፊት መደራጀትን፣ ተደራጅቶም መስዋዕትነትን፣ በሀገር ላይ ለውጥ የማየት ልባዊ ስሜትን ይጠይቃል! በተግባር ሳይሆን አሉባልታዊና ሐሜተኛ ማህበረሰብ እየተገነባ ከመጣ የመዝቀጥ አሊያም የመስበስ ክፉ አባዜ መምጣቱን ይጠቁማል (Decadence እንዲሉ)፡፡ ተግባራዊና የሚለውን የሚተረጉም ማህበረሰብ ካልፈጠርን ሟርት ይበዛል፡፡ “የማይወርስ ጐረቤት በሟርት ይገድላል” ይላል የወላይታ ተረትና ምሣሌ፡፡ ይሄንኑ ሁኔታ በቅጡ ሊነግረን ፈልጐ ነው፡፡

               ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚያደርጓቸው የተቃውሞ ሰልፎች ተደጋጋሚና መንግስት አቋም የያዘባቸውን ጉዳዮች የሚያነሱ እንደሆኑ የጠቆሙት ጠ/ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ፤ መንግስት ለእያንዳንዱ ሰልፍ ጥበቃ ማድረግ ስለማይችል ሰልፎቹ በተለመደው መልኩ ላይቀጥሉ እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡ ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ ትናንት በጽ/ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎቹ የሚያነሷቸው ጥያቄዎች የራሳቸው የፓርቲዎቹ ሳይሆኑ የሌሎች ሃይሎች እንደሆኑ ገልፀዋል፡፡

ፓርቲዎቹ ሰልፍ ማካሄድ ህገመንግስታዊ መብታቸው መሆኑን የጠቀሱት ጠ/ሚኒስትሩ፤ መንግስት በተደጋጋሚ ጥበቃ ሲያደርግ ቢቆይም፣ በሰልፎቹ የሚነሱት ጥያቄዎች ፋይዳ ቢስ ከመሆናቸውና ከፓርቲዎቹ ብዛት አንፃር መንግስት በቀጣይ ለሰልፎች ጥበቃ ለማድረግ የሚቸገርበት ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚችል አስረድተዋል፡፡

 ተቃዋሚ ፓርቲዎች፤ መንግስት በተደጋጋሚ ምላሽ የሰጠባቸውን ጥያቄዎች መላልሰው የሚያቀርቡት በመንግስት ላይ ጫና በመፍጠር አቋሙን ለማስቀየር በማሰብ ሊሆን ይችላል ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ይሄ ግን በፍፁም የማይሳካ ሃሳብ ነው ብለዋል፡፡ “ግንቦት ሰባት” በቅርቡ መንግስትን ለመጣል ወታደራዊ እርምጃ እንደሚወስድ በይፋ መግለፁን በተመለከተ ተጠይቀው ሲመልሱም፣ የፓርቲው አመራሮችና ደጋፊዎች ተጨባጭ ያልሆነ ህልም ውስጥ ሆነው የተናገሩት ነገር እንደሆነና ከህልማቸው ሲነቁ እውነታውን እንደሚገነዘቡት ጠ/ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡ ኢህአዴግ ውስጥ መከፋፈልና የሃይል መጠባበቅ አለ የሚለውን መረጃ በተመለከተም “ይህ የአንዳንድ አፍራሽ ሃይሎች ከንቱ ምኞትና ተጨባጭ ያልሆነ አሉባልታ ነው” ሲሉ አጣጥለውታል፡፡

የ3 ወሩ ህዝባዊ ንቅናቄ “ዋጋ የተከፈለበት” ነው ብሏል

                  ባለፉት ሶስት ወራት “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል የመጀመሪያ ዙር ህዝባዊ ንቅናቄ ሲያደርግ የቆየው አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ፤ ባለፈው እሁድ የማጠቃለያ ሰልፉን ሲያደርግ ደርሶብኛል ላለው የሞራልና የንብረት ጉዳት የአዲስ አበባ አስተዳደርና ፖሊስን በህግ እንደሚጠይቅ አስታወቀ፡፡ አንድነትና 33ቱ ፓርቲዎች ከትላንት በስቲያ በአንድነት ፅ/ቤት በሠጡት መግለጫ፤ የህዝባዊ ንቅናቄ ማጠቃለያ ሰልፉን መስከረም 19 አዲስ አበባ ላይ ለማካሄድ እንደምንችል የሚያረጋግጥ የእውቅና ደብዳቤ የከተማ መስተዳደሩ የከንቲባ ፅ/ቤት ቢሰጣቸውም፣ በእጅ አዙር ሠልፉ በመስቀል አደባባይ እንዳይደረግ መከልከላቸውን፣ ከህግ ውጪ በፀጥታ ተቋማት አካባቢ ሰልፉ እንዲከናወን መገደዳቸውንና ቅስቀሣ እንዳይደረግ መታገዳቸውን አመልክተዋል፡፡

ፖሊስም ህገ መንግስቱንና ህዝቡን መጠበቅ ሲገባው “ለመቀስቀስ፣ ፖስተር ለመለጠፍና በራሪ ወረቀቶችን ለማሠራጨት ፈቃድ ያስፈልጋል፣ ትዕዛዝ አልደረሠንም” በማለት ህገ መንግስታዊ መብቶችን ጥሷል ያሉት ፓርቲዎቹ፤ የአንድነትን ሊቀመንበር ጨምሮ 101 አባላትን ከማክሠኞ እስከ እሁድ ማሠሩንም ገልፀዋል፡፡ “ፖሊስ ለህግ የበላይነት መቆም ሲገባው በድብቅ ለተሠጠው ትዕዛዝ ተገዢ በመሆኑ ጉዳዩን ለህግ እናቀርባለን” ብለዋል - ፓርቲዎቹ፡፡ የፓርቲው አመራር አባል አቶ አስራት ጣሴ በተለይ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ቃለምልልስ፤ ስለ ሠላማዊ ሠልፍና ህዝባዊ ስብሠባ ማድረግ የወጣው አዋጅ “ማንኛውም ሠላማዊ ሠልፍ ወይም ህዝባዊ የፖለቲካ ስብሠባ በጦር ሃይሎች፣ በጥበቃ እና የህዝብን ሠላምና ደህንነት በሚቆጣጠሩ የመንግስት የስራ ክፍሎች አካባቢ 300 ሜትር ክልል ውስጥ ሊደረግ አይችልም” እንደሚል ጠቅሠው፤ የአዲስ አበባ መስተዳደር የአዋጁን አንቀፅ በመጣስ፣ እነዚህ ተቋማት በሚገኙበት ጃንሜዳ እንድንሰባሠብ ሊያስገድደን ሞክሯል ብለዋል፡፡ ፓርቲው ያቀረባቸውን ዘጠኝ ያህል አማራጭ ቦታዎች በመከልከል አዋጁን በጣሠ መልኩ በጃንሜዳ አድርጉ የሚል ትዕዛዝ ማስተላለፉ ከፍተኛ የህግ ጥሠት መሆኑን የጠቀሱት አቶ አስራት፤ ፓርቲው ያቀረባቸውን አማራጭ ቦታዎች ገምግሞ አለመፍቀዱም ሠላማዊ ሠልፍ የማድረግ ህገ መንግስታዊ ድንጋጌውን የጣሠ በመሆኑ በአስተዳደሩ ላይ ክስ እንመሰርታለን ብለዋል፡፡

ፓርቲው በፖሊስ ተቋማት ላይ የሚያቀርበው ክስ የተሻሻለውን የፓርቲዎች የምዝገባ አዋጅ መሠረት አድርጐ ነው ያሉት አቶ አስራት፤ አዋጁ የህዝብን የፖለቲካ ግንዛቤ ማዳበር፣ የፓርቲውን አላማ ለህዝብ ማስረፅ እንዲሁም ዜጐች በሃገሪቱ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ንቁ ተሣትፎ እንዲኖራቸው መቀስቀስ… የፖለቲካ ፓርቲ የዕለት ተዕለት ተግባራት መሆናቸውን እንደሚገልጽ ጠቅሰው፤ የአዲስ አበባ ፖሊስ አዋጁን በመጣስ በዚህ ሠላማዊ ሠልፍ ብቻ ከ100 በላይ ሠዎችን አስሯል ብለዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መኪና፣ ሞንታርቦና ጀነሬተር የመሣሠሉትን የፓርቲው ንብረቶችን ያለ አግባብ ስላገደ፣ በሁለቱም የመብት ጥሰቶች እንከሳለን ብለዋል፡፡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳየች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል ከእሁዱ ሠላማዊ ሠልፉ በኋላ ለመንግስት መገናኛ ብዙሃን በሠጡት መግለጫ፤ “ፓርቲው ባካሄደው የተቃውሞ ሠልፍ ላይ በሽብር ወንጀል ተከሠው የተፈረደባቸውን ግለሠቦች አቋም ማንፀባረቁና ማወደሱ የህግ መዘዝ ያመጣል፤ ፓርቲው ለሚመጣው የህግ መዘዝ ዝግጁ መሆን አለበት፡፡” ማለታቸው ይታወሳል፡፡

አቶ አስራት የአቶ ሽመልስ ከማልን መግለጫ በተመለከተ ሲናገሩ፤ “የህግ ጥሠት የፈፀሙት የመንግስት አካላት ስለሆኑ መከሠስ ያለባቸው እነሡ ናቸው፤ ከዚያ የተረፈው ዝም ብሎ ማስፈራራት ነው፤ እኛ ግን በሃገራችን አንፈራም፣ ልንፈራም አይገባም” ብለዋል፡፡ ከሠኔ 12 ቀን 2006 ጀምሮ እስከ መስከረም 19 ቀን 2006 በቆየው የሶስት ወር ህዝባዊ ንቅናቄ ፓርቲው በጐንደር፣ በደሴ፣ በባህር ዳር፣ በአርባ ምንጭ፣ በጅንካ፣ በአዳማና በፍቼ አባሎቹ እየተደበደቡና እየታሠሩም ቢሆን የተቃውሞ ሠልፎቹን ማካሄዱን ጠቅሶ፤ በመቀሌና በባሌ ሮቤ ጫናውን መቋቋም ባለመቻሉ ሣይካሄድ መቅረቱን አመልክቷል፡፡ በከፍተኛ ጫና ውስጥ ታልፎ የተደረገው ህዝባዊ ንቅናቄ የእስር፣ የድብደባ፣ የሞራል ጉዳትና የንብረት ማጣት ዋጋ የተከፈለበት እንደሆነ ፓርቲው አስታውቋል፡፡