Administrator

Administrator

ሺጉሜን የተባለው የጃፓን ንጉሥ ቻ-ኖ-ዩ የተባለው የሻይ ስነስርዓት በጣም ደስ ይለው ነበር፡፡ በችሎቱ ላይ ዳኛ ሆኖ ሲቀመጥ እንኳ ሻዩን እያደቀቀ ይፈጭ ነበር ይባላል፡፡ ምክንያቱ የሚከተለው ነው፡- 

ከዕለታት አንድ ቀን የሻይ ነጋዴ የነበረ ወዳጁን
“ህዝቡ ስለ እኔ ምን ያስባል?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ ነጋዴውም፤
“ማስረጃቸውን በግልፅ የማያቀርቡ ሰዎችን ትቆጣለህ፡፡ ሙልጭ አድርገህም ትሳደባለህ የሚል አስተያየት ነው ያለው፡፡ በዚህ ምክንያትም ህዝቡ እውነተኛውን ህጋዊ ማንነቱንና ጉዳዩን ወደ አንተ ለማቅረብ ስለሚፈራ እውነቱ በግልፅ አይታወቅም” ሲል ይነግረዋል፡፡
ንጉሡም፤
“አመሰግናለሁ! እንኳን ነገርከኝ፡፡ እኔ እስከዛሬ፤ ለሰዎች እቅጩን የመናገር ልማድ ነበረኝ፡፡ ስለዚህም ትሁቶቹና በድፍረት በአደባባይ የመናገር ድፈረት የሌላቸው ጨዋ ሰዎች እውነቱን ፍርጥ አድርገው አይገልፁም፡፡ ወደፊት ጠባዬን ማረም ይኖርብኛል” ይላል፡፡
ከዚህ በኋላ ንጉሡ ዙፋን ችሎት በሚቀመጥበት ጊዜ ሁሉ፤ አንድ የሚያስገርም ነገር ማድረግ ጀመረ ይባላል፡፡ በጨርቅ ተሸፍኖ የሻይ መውቀጫው/መፍጫው ከስሩ እንዲቀመጥለት ያዛል፡፡ በሀር ጨርቅ ተሸፍኖ ጥዋ መስሎ ይቀመጥለታል፡፡ ከዚያም አቤቱታ አቅራቢው ህዝብ አቤቱታውን ሲያሰማ እሱ ሻዩን እየወቀጠ ትኩረቱን ወደ ሙቀጫው በማድረግ ቁጣውን ይቆጣጠራል፡፡
ቀጥሎም የፈጨውን ሻይ በትክክል መድቀቅ አለመድቀቁን በእጁ እየነካ ያየዋል፡፡ ያረጋግጣል፡፡ ሻዩ በትክክል ከተፈጨ መንፈሱ የረጋና ሚዛናዊ መሆኑን ያስባል፡፡ በትክክልም አቤቱታ ማዳመጡን ያምናል፡፡ ሻዩ ያላግባብ የተወቀጠ ከሆነ ግን የተረበሸና ቁጠኛ ስሜት እንደነበረው ያውቃል፡፡
በረጋ መንፈስ የተፈጨው ሻይ፤ ፍርድ በትክክል መስጠቱንና አቤት ባዮቹም ረክተው መሄዳቸውን ይነግረዋል፡፡ ይሄኔ፤
“ተመስገን! ህዝቤ ሳያዝንብኝ፤ ረክቶና ደስ ብሎት ሄዷል ማለት ነው” ብሎ ፈገግ ይላል፡፡
* * *
ለህዝብ የሚቆረቆር ዕውነተኛ መሪ የህዝብን ብሶት ማዳመጥ፤ አቤቱታውን መስማት ያረካዋል። ህዝብ የልቡን ዕውነት የሚደብቅ ከሆነ ትክክለኛ አስተዳደር አለ ለማለት ያዳግታል፡፡ ዐይና - ውጣው በአደባባይ እንደልቡ ሲናገር፤ ጭምቱና ፈሪው ሃሳቡን ሳይገልጽ ይቀራልና ሥርዓቱ ሁሉንም ያስተናግዳል ለማለት አያስደፍርም፡፡ ሃሳቡን የሚገልጽ ህዝብ የዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ምሰሶ ነው። በዚህ ረገድ በጥሞና የህዝብን የልብ ትርታ ለማዳመጥ የሚችል ጆሮ ያለው መሪ ያስፈልጋል፡፡ የመሥሪያ ቤት አለቃ፣ የማህበር መሪም ሆነ የፖለቲካ መሪ አስተዋይ አዕምሮ፣ ሆደ - ሰፊ አመራርና “ወደፊት ይህን ይህን ጠባዬን ማረም ይኖርብኛል” የማለት ድፍረት ሊኖረው ያሻል፡፡ ያን ካገኘን ታድለናል፡፡
የአንድ ሀገር ህዝብ እንደዜጋ የተፃፈን ጽሑፍ በነፃነት፣ በጥሞናና በጥንቃቄ አንብቦ የሚመረምር፤ ያሻውን ዓይነት የፖለቲካ ሥርዓት የሚከተል፣ በነፃነት አገዛዙን የሚቃወም፣ የሚተችና ሲያስፈልግ አይሻኝም የማለት መብቱን የሚያውቅ ሊሆን ይገባል፡፡ እንደአራሽ እንደላብ - አደርም የአቅሙን ያህል ማምረትና የኢኮኖሚ ህልውናውን ሊያጠናክር ይጠበቅበታል፡፡ እንደዜጋም ሆነ እንደሠራተኛ በአገሩ ይኖር ዘንድ የሚያሠራው፣ የሚያሳትፈው ሥርዓትና ህግ ሊያገኝም የግድ ነው፡፡
“ባገር እኖር ብዬ
ልጅ አሳድግ ብዬ
ከብት እነዳ ብዬ፤
ለባሻ ዳርኩለት ሚስቴን እቴ ብዬ”
እያለ የሚያለቅስ ባላገር በምንም ዓይነት ማየት የለብንም፡፡ ጊዜውም ቦታውም አይፈቅድምም። በፖለቲካ የተገፋ፣ በኢኮኖሚ የደቀቀ፣ ማህበራዊ ድርና ማጉ ውሉ የጠፋ ህብረተሰብ እንዳይኖር ነው የስትራቴጂያችን ዒላማ! ውሃ ጋ ከሆን አሣ፣ ግጦሽጋ ከሆን ሥጋ መብላትን ልናውቅበት ወቅቱ ያስገድደናል፡፡
አንድ የገዛ በሬው ሊወጋው የሚያሳድደው ባለበሬ ለአንድ የሰፈር አዛውንት፤ “እረ ይሄ በሬ እያሳደደ አስቸገረኝ“ ቢላቸው፤ “የት ነው የምትተኛው?” ብለው ጠየቁት አሉ፡፡ ባለበሬውም፤ “ቤቴ። ሣር ፍራሼ ላይ!” ይላቸዋል፡፡ ሽማግሌውም፤
“ታዲያ ቀለቡ ላይ እየተኛህ ዱሮስ ላያባርርህ ኖሯል እንዴ?” አሉት ይባላል፡፡ ሰውንም ቀለቡ ላይ ተኝተን ነፃነት አለህ ብንለው የለበጣ ነው የሚሆነው፡፡ ነፃነቱን ከኢኮኖሚ ጥቅሙ የሚያስተሳስር ሥርዓት መፍጠር ተገቢ ነው፡፡ ለተገቢ ሥርዓት ክሳቴ የሚታገሉ ሁሉ ጊዜን መሠረት ያደረገ ስትራቴጂ ይኖራቸው ዘንድ ወቅቱ ይጠይቃቸዋል፡፡
“ፊት የበቀለን ወፍ ይበላዋል” የሚለውን ተረት ሳንረሳ “የዘገየ ፍርድ ካልተፈረደ አንድ ነው”ን እያውጠነጠንን፤ ትክክለኛው ጊዜ ሲደርስ ግን “የሚሥማሩን አናት መምታት”ና አጋጣሚን በአግባቡ መጠቀም ወሳኝ መሆኑን ልናሰምርበት ይገባል፡፡ በወቅቱ ያልዘራም በወቅቱ ያልሰበሰበም ሁለቱም ከመራብና ከማስራብ አይድኑም - “ንገሥ ቢሉት ዛሬ ሰምበት ነው አለ” የሚለው የጉራጊኛ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው!!

ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ በድጋሚ ተቀጠረ

በዓዲ ኀትመትና ማስታወቂያ ሓላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ስም እየታተመ የሚወጣው “አዲስ ታይምስ” መጽሔት፤ ከብሮድካስት ባለሥልጣን የሞያ ብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀት እድሳት በመከልከሉ ከኅትመት ውጪ ሆነ፡፡ አሳታሚው ለዝግጅት ክፍላችን እንደገለጸው፤ የአገሪቱ የፕሬስ ሕግ በሚያዘው መሠረት የመጽሔቱን ዓመታዊ ፈቃድ ለማሳደስ ከድርጅቱ የሚጠበቁትን መስፈርቶች ሙሉ በሙሉ ቢያሟላም የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን ጥር 2 ቀን 2005 በላከው ደብዳቤ ለመጽሔቱ የሞያ ብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት እድሳት እንደማያደርግ አስታውቋል፡፡ የኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን እድሳቱን እንደማያደርግ ለአሣታሚው በላከው ደብዳቤ ያመለከተው ሦስት ዋና ዋና ምክንያቶችን በመጥቀስ ነው። እነዚህም የአክስዮን ባለቤቶችና የአድራሻ ለውጥ ሲደረግ በ15 ቀን ውስጥ ለባለሥልጣኑ ማሳወቅ አለመቻል፣ ለኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት መወዘክር የዐሥራ አምስት ቀን እትም አለማስገባት እንዲሁም መፅሔቱ “በሕጋዊ ባለቤቶቹ ሳይሆን ምንጩ በማይታወቅ ገንዘብ ነው የሚተዳደረው የሚሉት ናቸው፡፡ የ“አዲስ ታይምስ” መፅሔት ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን በበኩላቸው፤ የአክስዮን ባለቤትነት እና የአድራሻ ለውጥ ሲያደርጉ በጊዜው በደብዳቤ ማሳወቃቸውን፣ በየዐሥራ አምስት ቀኑ ለኢትዮጵያ ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ሁለት ሁለት ኮፒ ያስገቡበትን ደረሰኝ ለባለሥልጣኑ ማቅረባቸውን አስረድተዋል፡፡ ‹‹ማንነቱ በማይታወቅ የገንዘብ ምንጭ ነው የሚንቀሳቀሰው›› የሚለውን የባለሥልጣኑን ምክንያት ደግሞ “በጥንቆላ ላይ የተመሠረተ መረጃ ነው” ሲሉ አጣጥለውታል፡፡ “ጉዳዩን ይዘን ወደ ፍርድ ቤት እናመራለን” ያሉት አቶ ተመስገን፤ የመጽሔቱ መታገድ ‹‹የአቶ ኀይለማርያም መንግሥት የመለስን ራዕይ እናስቀጥላለን ሲል የነበረውን በተግባር እያረጋገጠ መሆኑን ያመለክታል” ብለዋል፡፡ የአራት ወራት ዕድሜ ያስቆጠረው “አዲስ ታይምስ” መጽሔት ከ35 ሺሕ ኮፒ በላይ እየታተመ በየሁለት ሳምንቱ ይሠራጭ እንደነበር፣ ይህም በአገሪቱ ካሉ መጽሔቶች በኅትመት፣ ብዛትና በተደራሽነት ቀዳሚ እንደሚያደርገው አቶ ተመስገን ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡

በኢትዮጵያ ብሮድካስት ባለሥልጣን የሕዝብ ግንኙነት ተጠባባቂ ሓላፊ የሆኑት አቶ ወርቅነህ ጣፋ በበኩላቸው፤ ባለሥልጣኑ የእድሳት ክልከላውን ከማድረጉ በፊት ከባለአክሲዮኖቹ ጋር የአድራሻ ቅየራ እና የአክሲዮን ድርሻ ለውጥ ሲደረግ አለማወቃቸው እንዲሁም በቤተ መጻሕፍት ወመዘክር የመጽሔቱ ቅጂዎች እየደረሱ እንዳልሆኑ ተወያይተንባቸው ችግሩ እንዳለ አምነው ተቀብለው ነበር ብለዋል፡፡ የመጽሔቱ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ተመስገን ደሳለኝ፤ የአክስዮኑ 93 በመቶ ድርሻ ባለቤት አገር ውስጥ እንዳልሆኑና ሰባት በመቶ ድርሻ ያላቸው ግለሰብ ብቻ አገር ውስጥ መኖራቸውን በመግለፅ አገር ውስጥ ያሉትን ብቻ አነጋግሮ እዚህ ድምዳሜ ላይ መድረስ እንደማይቻል ተናግረዋል፡፡ አቶ ወርቅነህ የፋይናንስ ምንጩን በተመለከተ ሲናገሩ፤ ‹‹አሁን በግልፅ ይፋ ባናደርግም መረጃው አለን” ብለዋል፡፡ ይህ በዚህ እንዳለ የሕዝብን ሐሳብ ማናወጥ፣ ሕዝቡን በሕገ - መንግሥቱ ላይ ማነሣሣትና የመንግሥትን ስም ማጥፋት የሚሉ ሦስት ክሦች የተመሰረተባቸውና ነሐሴ 17 ቀን 2004 ዓ.ም በቃሊቲ ማረሚያ ቤት ለስድስት ቀናት ከታሰረ በኋላ ክሱ ተቋርጦ በነጻ የተለቀቁት የቀድሞው የፍትሕ ጋዜጣ ዋና አዘጋጅ አቶ ተመስገን ደሳለኝ፤ ከሦስት ወር በኋላ ክሱ በዐቃቤ ሕግ ተንቀሳቅሶ በ50ሺሕ ብር ዋስ መለቀቃቸው ይታወሳል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት 16ኛ ወንጀል ችሎት ትእዛዝ ታኅሣሥ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ቀርበው ተለዋጭ ቀጠሮ የተሰጣቸው የድርጅቱ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማስተዋል ብርሃኑ እና የጋዜጣው ዋና አዘጋጅ አቶ ተመስገን ደሳለኝ ትላንት ጥር 23 ቀን 2005 ዓ.ም ቢቀርቡም “መዝገቡን አልመረመርነውም” በሚል ብይኑ ሳይሰማ የቀረ ሲሆን ችሎቱ ለየካቲት 1 ቀን 2005 ዓ.ም እንዲቀርቡ ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡

የዘፍጥረት ሁለት ትረካዎች ተመሳሳይ አይደሉም? በየዘመኑና በየሃይማኖቱ የሚነገሩ የውኃ ጥፋት ትረካዎችስ?

ወደ ዙፋን የሚወጣ ንጉስ፤ ነባር ስሙ ይቀየራል። ዘውድ የሚደፋው በቀድሞ ስሙ አይደለም- አዲስ ስም ይወጣለታል - ተፈሪ መኮንን፣ አፄ ኃይለሥላሴ እንደተባሉት። ወይም ካሮል ዎይትላ፣ የሮም ካቶሊቅ ጳጳስ የሆኑትም ጆን ፖል በሚል ስያሜ ነው። የአሁኑ ጳጳስ ቤኔዲክት ደግሞ፤ ጆሴፍ ራትዚንገር ነበር ስማቸው። ንግስናም ሆነ ጵጵስና እንደገና እንደመወለድ፤ አልያም የቀድሞው ማንነት ሞቶ በአዲስ መልክ እንደመነሳት ስለሚቆጠር፣ አዲስ ስም ይጎናፀፋሉ። ወደ አዲስ ሃይማኖት የሚገባ ሰው ላይም ተመሳሳይ የስም ለውጥ ይከሰታል። ለምሳሌ የሚጠመቅ ሰው፤ በፈጣሪው ዘንድ ለሁለተኛ ጊዜ እንደተወለደ ወይም ሞቶ እንደተነሳ ይታመን የለ? እናም ሰዎች ሲጠመቁ አዲስ ስም ይወጣላቸዋል። ከ4000 አመት በላይ እድሜ ያስቆጠረው የግብፃዊያኑ ሃይማኖትም እንዲሁ በዳግም ልደትና በጥምቀት፣ በሞትና በትንሳኤ ዙሪያ ያጠነጠነ ነበር - የስም ለውጥ ጭምር። ልደትና ጥምቀት፣ ንግስናና የ30 አመት ህዳሴ፣ ሞትና ትንሳኤ ጥንታዊዎቹ ግብፃዊያን፣ “የሰማያት አምላክ፣ የምድር ንጉስ” እያሉ የሚያመልኩት ሆረስ፣ በአካል ግብፅን እንደገዛ ይነገርለታል። ከሞተ በኋላም ከዙፋን አልወረደም ማለት ይቻላል። ከሱ በኋላ የነገሱ ሁሉ፣ የሆረስ አምሳል እንደሆኑ ይታመንባቸዋልና - የሆረስ ዙፋን ላይ የተቀመጡ አዲስ ሆረስ እንደማለት ነው። ግብፅን የሚገዛ ፈርኦን፣ በምድር ላይ በስጋ የተገለፀ ሆረስ ነው ይባልለታል (በአካል የመጣ አምላክ)። ታዲያ ፈርኦኑ፤ ንጉስ ብቻ ሳይሆን፤ የሃይማኖት መሪም ጭምር መሆኑ ምኑ ይገርማል? የቤተመቅደስ ራስ ነው - High Priest ይሉታል (በብሪቲሽ ሙዚየም የተዘጋጀው Dictionary of Anciet Egypt ገፅ 228)። እንደ እንደ ሊቀ ጳጳስ ነው ማለት ይቻላል። ፈርኦኑ ወይም እንደራሴው በ12 አጃቢና ረዳት ቀሳውስት ጋር የአገሬውን የአይማኖት እምነት ይመራል። እንግዲህ ከአምላክ የተወለደው ሆረስ በግብፅ ምድር በአካል ንጉስ ነበረ ተብሎ ይታመንበት የለ? የሃይማኖትም መሪ ነበር - ንጉስም ሊቀጳጳስም እንደማለት። 12 አጃቢ ቀሳውስት ይኖሩታል። (የአማልክት ጌታ አሞን ወይም ራዕ በአስራ ሁለት አጃቢ አማልክት ተከብቦ እንደሚታየው ማለት ነው።) ከ3500 አመት በፊት በሕንፃዎች ላይ የተቀረፁ ፅሁፎች ናቸው ይህንን የሚመሰክሩት። ANCIENT RECORDS OF EGYPT በሚል ርዕስ University of CH ICAGO ያዘጋጀው መፅሐፍ ውስጥ ተተርጉመው ከቀረቡት ጥንታዊ የግብፅ ሃይማኖታዊ ትረካዎች መካከል ቀንጭቤ ላካፍላችሁ። ፅሁፉ የንግሥና በአልን ይተርካል። በእርግጥ ንግስናው ያልተለመደ ነው። ሴት ነች የምትነግሰው። እንዴት ተደርጎ? እንዴት ነው አንዲት ሴት እንደ ወንድ ሆረስን ሆና በሆረስ መንበር የምትቀመጠው? ከፅሁፎቹ የምናገኘው መልስ ቀላል ነው። ከአምላክ ተወልዳ፣ እንደ ወንድ ሆና ነው የምትነግሰው። ንግስት ተብላ ሳይሆን ንጉስ ተብላ! ለዚያውም እንደ ሌሎቹ ፈርኦኖች የውሸት ፂም መሰል ነገር አገጯ ላይ አንጠልጥላ። ለማንኛውም ፅሁፉ እንዲህ ይላል። Amon-Re enthroned at the right, before twelve gods in two rows at the left. (የሰማያት ዙፋን ላይ ከተቀመጠው የአማልክት ጌታ አሞን-ራዕ ጎን 12ቱን አማልክት የሚያሳይ ስዕል ከፅሁፉ አጠገብ አለ)። ግብፅን ለመግዛት የታጨችው ሴት የፈርኦን ልጅ ብትሆንም፤ አሞንራዕ “የኔ ልጅ ናት” ይላል። ፈርኦኖች ሁሉ አምላክን የሚወክሉ ናቸዋ። የሆነ ሆኖ አሞንራዕ እንዲህ ይላል፤ “ሁሉንም ግዛቶች፣ ሁሉንም አገራት እሰጣታለሁ። መንፈሴ ከውስጧ አለ፣ በረከቴ እሷ ላይ ነው,... ዘውዴ ከሷ ጋር ነው።

ሰሜኑንና ደቡቡን ትገዛለች፣ ሕያዋንን ሁሉ ትመራለች...” አሁን የምትታወቅበት hatshepsut የተሰኘው ስም የሚወጣላትም በዚሁ ጊዜ ነው። ንግስና ማለት እንደገና እንደመወለድ ይቆጠር የለ? እናም፣ ፈጣሪ አምላክ ሃትሸብሱትን በያኔዋ የፈርኦን ሚስት በእናቷ ማህፀን ውስጥ በማስገባት እንድትወለድ ካደረገ በኋላ፤ “ስሟም፤ ክህነመት አሞን ሃትሸብሱት ይሆናል። ግዛቱን ሁሉ በላቀ ጥበብ የምትፈፅም ንግስት ትሆናለች” አለ። አሞንራዕ ደስ ብሎት፣ ለራሷ ለሃትሸብሱት እንዲህ ይላታል - “Glorious part which has come forth from me; king, taking the Two Lands, upon the Horus-throne forever.” “ከኔ የተፈለቅሽ ቅዱስ አካል። ሁለቱን ምድሮች የምትወስጂና በሆረስ ዙፏን ለዘላለም የምትቀመጪ ንጉስ!” ይላታል። ንግስት ሳይሆን ንጉስ አላት - እንደ ሆረስ ነዋ መቆጠር ያለባት። ሆረስ በሌላ አካል የመጣ ያህል ነው። የሷ ንግግሮችም ይህንን የተከተሉ ናቸው። አንደኛ ራሷን ንጉስ ትላለች - ራሷን እንደሆረስ በመቁጠር። ሁለተኛ ራሷን የንጉስ ሚስት ትላለች። ንጉስም የንጉስ ሚስትም ናት። የምድር አባቷን (ቱስሞስን) ኦሲሪስ ብላ ትጠራዋለች፤ እናቷን (አሞስን) ደግሞ ኢሲስ ብላ ትጠራታለች። ኦሲሪስና ኢሲስ ግን የሆረስ ወላጆች ናቸው። በሃትሸብሱት፣ የንግስና በዓል ላይ ሁለት ነገሮች ይፈፀማሉ። እንግዲህ፤ የግብፅ ፈርኦን በ30 አመት ንግስናው እንደሞተ ይቆጠር የለ? “በ30 አመቱ ተጠመቀና እንደገና ተወለደ። በህዳሴ ከሞት ተነሳ” ተብሎ እሱ ራሱ በስልጣኑ ላይ ሊቀጥል ይችላል። አብዛኛውን ጊዜ ግን፤ በንጉሱ አምሳል ልጁ ይነግሳል - በጥምቀት እንደገና ተወለደ ተብሎ፣ ከሞት ተነሳ ተብሎ። ሃትሸብሱትም እንዲሁ በአባቷ ምትክ ዙፋን ላይ እንድትወጣ፤ የምድር አባቷ ዘውድ ሲደፋላት ይታያል - (ስዕል ላይ ስትታይ ወጣት ናት)። በሌላ በኩል ደግሞ፤ በአማልክት ፊት ትጠመቃለች፤ የአማልክት ጌታ አሞንራዕ በላይዋ ላይ ውሃ እያፈሰሰ ያነፃታል (በስዕል ላይ ስትታይ ህፃን ነች። መጠመቅና ንግስና እንደገነና ነፅቶ መወለድን ያመለክታል ብለው ስለሚያምኑ)። በጥምቀቱ ላይ፤ የአሞን ራዕ 12 አጃቢ መላእክት በአንድነት ይናገራሉ፤ “ከታችኛውና ለላይኛው ግብፅ ታላቅ የንጉስ ክብር፣ ከነፍስሽ ጋር ነፅተሻል (ነፅተሃል)” ይላሉ። “ወርቃማ ሆረስ... የላይኛውና የታችኛው ግብፅ ንጉስ” የሚል ተጨማሪ ስም ይወጣላታል። የወንድ ንጉሥ ልብስ አድርጋ ንግስናዋ ሲታወጅም በስዕል ይታያል። ንጉሥ ብቻ ሳትሆን የአምላክ ተወካይም ነችና፤ እንደ ሊቀ ጰጳስ ነች - እንደ ሆረስ (12 ቀሳውስት የሚያጅቡት ሊቀ ቀሳውስት)።

ANCIENT RECORDS OF EGYPT V.2 ከገፅ 202 - 292። እንግዲህ፤ የአምላክ ልጅነትና ንግስና፣ ውልደትና የሰላሳ አመት ጥምቀት፣ የሞትና የትንሳኤ ... በጥንታዊያኑ የግብፅ ሃይማኖት ውስጥ ምን ያህል ቦታ እንዳለው ከዚህ ትረካ ማየት ይቻላል። የሆረስ ታሪክ ከኢየሱስ፣ ከሚትራ፣ ከክሪሽና፣ ከዲኖስየስ ጋር ይመሳሰላል የሚባልበት አንዱ ምክንያትም ከእንደዚህ አይነት ትረካዎች የተነሳ ነው። በእርግጥ፤ “ምንም ተመሳሳይነት የለም” ብሎ መሸምጠጥም ይቻላል። ነገር ግን፤ የልዩነቶች መኖር ተመሳሳይነትን አያስቀርም። ለልዩነት ለልዩነትማ፤ በዘፍጥረት ምዕራፍ አንድ እና ሁለት መካከልም በርካታ ልዩነት አለ። የዘፍጥረት ሁለት ትረካዎች አንደኛው ትረካ፡ ዘፍጥረት ምዕራፍ 1 ላይ፤ መጀመሪያ ቀንና ሌሊት፣ በሁለተኛው ቀን ሰማይን፣ በሶስተኛው ቀን ምድርና ባህርን እንዲሁም እፀዋትን፣ በአራተኛው ቀን ፀሐይ፣ ጨረቃና ኮኮቦችን ፈጠረ። በአምስተኛው ቀን፤ ከውኃ የባሕር እንሰሳትንና በራሪ አእዋፋትን ፈጠረ። በስድስተኛው ቀን ከምድርም አራዊትን ፈጠረ። በመጨረሻም ሰውን በእግዚአብሔር መልክ ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው። እናም ባረካቸው፤ “... የባሕርን ዓሦችና የሰማይን ወፎች በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ግዙአቸው። ...እነሆ መብል ይሆናችሁ ዘንድ በምድር ፊት ሁሉ ላይ ዘሩ በእርሱ ያለውን ሐመልማል ሁሉ፥ የዛፍን ፍሬ የሚያፈራውንና ዘር ያለውንም ዛፍ ሁሉ ሰጠኋችሁ። ለምድርም አራዊት ሁሉ፥ ለሰማይም ወፎች ሁሉ፥ ሕያው ነፍስ ላላቸው ለምድር ተንቀሳቃሾችም ሁሉ የሚበቅለው ሐመልማል ሁሉ መብል ይሁንላቸው” አለ። “እንዲሁም ሆነ። እግዚአብሔርም ያደረገውን ሁሉ አየ፥ እነሆም እጅግ መልካም ነበረ”... በሰባተኛው ቀን እረፍት ሆነ። ሁለተኛው ትረካ፡ በምዕራፍ 2 ላይ የምናገኘው ታሪክስ ምን ይመስላል? እስካሁን እግዚአብሄር እንዲህ አለ፣ እንዲህ አደረገ እያለ ሲተርክ የነበረው “ዘፍጥረት” ምዕራፍ 2 አንቀፅ 4 “እግዚአብሔር አምላክ...” የሚል አጠራር መጠቀም ይጀምራል። እናም ምድርና ሰማይ የተፈጠሩ ጊዜ፣ አንዳችው ቁጥቃጦና ቡቃያ በምድር ላይ እንዳልነበረ በመግለፅ የፍጥረት ትረካውን በአዲስ መልክ መልሶ ያቀርባል። የምድር ቡቃያ ያልነበረው ስላልዘነበ መሆኑን፤ የሚሰራበት ሰውም እንዳልነበረ ይገልፃል። በቀድሞው ትረካ ሰው (ወንድና ሴት) በእግዚአብሔር አምሳያ እንደተፈጠሩ ቢጠቀስም፤ አሁን ግን አዳምን ብቻ ከአፈር ይፈጥረዋል። “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት” ይላል። በኋላም “አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ” ይለዋል። ታዲያ ይሄ የእግዚአብሔር አምሳል ነው? የሆነ ሆኖ፤ አዳም ከተፈጠረ በኋላ በምር ላይ እፅዋት ያለበት አካባቢ (ገነት) ይፈጠርና አዳምን እዚያ ወስዶ ያስቀምጠዋል። ከሰው በፊት እፀዋትና እንሰሳት አልተፈጠሩም እንዴ? የመጀመሪያው ትረካ ላይ... አዎ። እና ደግሞ፤ የሁሉም ነገር ገዢ ሆኗል፤ ከቅጠሉም፣ ከፍሬውም፣ ከእንስሳውም ያሻውን መጠቀምና መብላት ትችላለህ የሚል ስልጣን ተሰጥቶታል። ገዢ ሆኗል። ትዕዛዝ አልተጫነበትም። በሁለተኛው ትረካ ግን በቅድሚያ ሰው ተፈጠረና፣ ከዚያ እፀዋት መጣ። እናም ትዕዛዝ ተከተለ። “እግዚአብሔር አምላክም ሰውን እንዲህ ብሎ አዘዘው። ከገነት ዛፍ ሁሉ ትበላለህ፤ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና”። ከዚያ፤ “እግዚአብሔር አምላክም የምድር አራዊትንና የሰማይ ወፎችን ሁሉ ከመሬት አደረገ” ይላል። በምዕራፍ 1 ላይ፤ እፀዋት ብቻ ሳይሆኑ፤ አራዊትን ከምድር፤ አእዋፍና የባሕር እንስሳትም ከውኃ የተፈጠሩት ከሰው በፊት ነው። በምዕራፍ 2 ትረካ ላይ ግን፤ ሰው በቅድሚያ መፈጠሩን እናነባለን። አእዋፋትም ከውኃ ሳይሆን ከመሬት መፈጠራቸውን ይነግረናል። ሁለተኛው ትረካ ላይ ያለ ሴት የተፈጠረው አዳም፣ ረዳት ያሻዋል ተባለና በተኛበት አንድ የጎድን አጥንቱ ተወስዶ ሴት ተሰራች። (ተፈጠረች፤ ተወለደች)። ከአጥንቴና ከስጋዬ የተገኘች ይላታት። ከዚያ ሚስቱ ትሆናለች። ... ገና ሚስቱ አልሆነችም። እንዲያውም፤ ወንድና ሴት መሆናቸው ግድ አልሰጣቸውም። አላወቁም። አይናቸው አልተከፈተም ነበር። ተንኮለኛው እባብ ነው፤ አይናቸው እንዲከፈት መዘዝ የሆነው። በገነት መሃል ካለው የዛፍ ፍሬ (መልካሙንና ክፉውን ለመለየት ከሚያስችለው ፍሬ) የበላ ይሞታል የሚል ትዕዛዝ ቢኖርም፤ እባብ ግን “አትሞቱም” ብሎ ለሴቷ ለሄዋን ይነግራታል። እንዳትበሉ የተከለከላችሁት፤ “በበላችሁ ቀን ዓይኖቻችሁ እንደሚከፈቱ፣ እንደ አማልክትም መልካምንና ክፉን የምታውቁ እንደምትሆኑ እግዚአብሔር ስለሚያውቅ ነው...” ብሎ ያግባባታል። በእርግጥ እባቡ እንዳለውም፤ ፍሬውን ሲበሉ፤ አልሞቱም፤ አይኖቻቸው ተከፈቱ፤ ወንድና ሴት መሆናቸውንም አወቁ። ደግሞም እንደ አማልክት ትሆናላችሁ ብሏቸዋልኮ። በእርግጥሞ ሆነዋል። ምዕራፍ ሁለት ማጠቃለያ እንዲህ ይላል። ... እግዚአብሔር አምላክም፤ እነሆ አዳም መልካምንና ክፉን ለማወቅ ከእኛ እንደ አንዱ ሆነ አለ። አሁንም እጁን እንዳይዘረጋ፥ ከሕይወት ዛፍ ወስዶ እንዳይበላ፥ ለዘላለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር፤ እግዚአብሔር አምላክ ከዔድን ገነት አስወጣው፥ የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ። በመጀመሪያው ምዕራፍ አተራረክ፤ አዳምና ሄዋን በአምላክ አምሳያ ነው ህልውና ያገኙት። በምዕራፍ 2 አተራረክ ግን፤ ምኑንም ምኑንም የማያዋቁ አዳምና ሄዋን፤ የተከለከለ የዛፍ ፍሬ ከበሉ በኋ ነው የአምላክ አምሳያ የሆኑት። ግን፤ የዘላለማዊነትን ዛፍ እንዳይበሉ ከገነት ተባረሩ። እንግዲህ፤ ከዚህ በኋላ ነው ባልና ሚስት የሆኑት። የኔ ጥያቄ የምዕራፍ 1 እና የምዕራፍ 2 ትረካዎች በርካታ ልዩነቶች ቢኖሯቸውም፤ ተመሳሳይነታቸው የጎላ አይደለም ወይ የሚል ነው። የቅደም ተከተልና የዝርዝር ነጥቦች ልዩነት ቢኖርም፤ ሁለቱ ትረካዎች መሰረታዊ ልዩነት የላቸውም ማለት ይቻላል። በአጭሩ፤ ነገሮቹን በሙሉ እግዚአብሔር እንዳሻው አድርጎ ፈጠራቸው የሚል ነው የሁለቱ ትረካዎች መሰረታዊ ሃሳብ። በዚያ ላይ፤ የተፈጠሩት ነገሮች ያው ተመሳሳይ ናቸው። ሰማይ፣ ምድርና ባሕር፣ እፀዋትና አራዊት፣ እና ሰው! በእርግጥ፤ የ3200 አመት እድሜ አስቆጥሯል በሚባለው ጥንታዊ የፔርሺያ የሃይማኖት መፅሐፍም ስለ ፍጥረት ይተርካል። አምላክ ሁሉን ነገር በ6 ወቅቶች እንደፈጠራቸው የሚገልፀው አቬስታ የተሰኘው ጥንታዊ ሃይማኖታዊ መፅሐፍ፤ በቅድሚ ሰማያት፣ ቀጥሎ ባሕሮች፣ ከዚያ መሬት፣ ከዚያ እፀዋት፣ ከዚያ እንሰሳት፣ በስድስተኛውም ወቅት ሰው እንደተፈጠረ ይተርካል። ... BIBLE MYTHS AND THEIR PARALLELS IN OTHER RELIGIONS (ገፅ 7)። ታዲያ ይሄኛው ትረካና የዘፍጥረት ትረካስ አይመሳሰልም? የኖህ ታሪኮች በየአገሩና በየሃይማኖቱ የኖህ ታሪክን ጨምሮ፣ የ”ባይብል” የመጀመሪያዎቹ አምስት መጻሕፍት፣ ከ2500 እስከ 3000 አመት እድሜ ካላቸው ሰነዶች የተዋቀሩ እንደሆነ የሚናገሩት ተመራማሪዎች፤ ቢያንስ የሁለት ሃይማኖታዊ ቡድኖች የተውጣጣ እንደሆነ ይናገራሉ። የሁለቱ ቡድኖች ትረካ በ”ዘፍጥረት” ተደራርቦ እንደቀረበው ሁሉ፤ በኖህ ታሪክም ላይ ሁለት ትረካዎች ይደጋገማሉ። መቼም የኖህ ታሪክ ቢያንስ በከፊል ምሳሌያዊ አነጋገር መሆኑ አያጠራጥርም። መጽሐፉ እንደሚለው፤ ኖህ ከአዳም በ10ኛ ትውልድ ነው። በ10 ትውልድ እንዴት ነው፤ አለም በሰው ልጆች ቆሻሻና ክፋት ተሞላች ሊባል የሚችለው? እንዲያ ከአዳም ጀምሮ ሁሉም በሕይወት ቢኖሩ እንኳ ቁጥራቸው አንድ ሚሊዮን አይደርስም። እንደ ኖህ ሶስት ልጆችን ወይም እንደ አዳም 6 ልጆችን የሚወልዱ ከሆነ ደግሞ በምድር ላይ የሰዎች ቁጥር በጣም ትንሽ መሆን አለበት። የሆነ ሆኖ ፈጣሪ በጎርፍ ከኖህና ከልጆቹ በቀር ሰዎችን ሊያጠፋ ስለወሰነ፤ ኖህ መርከብ እንዲሰራ ታዘዘ። በአንደኛው ትረካ፡ ኖህ ከምድር ተንቀሳቃሽ ፍጥረታት ሁሉ ሁለት ሁለት ከሴትና ከወንድ ወደ መርከብ እንዲያስገባ ተነገረው ይላል ዘፍጥረት 6፡20። ከእያንዳንዱ የእንሰሳ አይነት አንድ ወንድ አንድ ሴት ለምሳሌ አንድ በሬና አንድ ላም እንደማለት ይመስላል። ሁለት በሬ፣ ሁለት ላም የሚል ትርጉምም ሊኖረው ይችላል። ሁለተኛው ትረካ፡ ንፁሕ ከሆኑት እንሰሳትና አእዋፋት ሰባት ወንድ ሰባት ሴት፤ ንፁሕ ካልሆኑት ደግሞ ሁለት ሁለት ወደ መርከቡ ውስጥ እንዲያስገባ እንደታዘዘ ይገልፃል ዘፍጥረት 7፡2-3። ለምሳሌ ሰባት በሬ ሰባት ላም እንደማለት ነው። ፈጣሪ ለኖህ የሰጠው ትዕዛዝ የትኛውም ቢሆን፤ በሰባት ቀን ውስጥ የጥፋት ውኃው እንደሚጀምር ተነግሮታል። ዝናቡና ጎርፉ ለአርባ ቀንና ሌሊት አያቋርጥም ተብሏል። ኖህ፣ በታዘዘው መሰረት መርከብ ሰርቶ፣ በታዘዘው መሰረት እሱና ቤተሰቡ፤ እንዲሁም ከእንሰሳት ዘር ሁሉ ሰብስቦ አስገባ። ግን ሰባት ሰባት እየሆነ የገባ የእንሰሳ አይነት እንደሌለ ይገልፃል።

በመፅሐፉ መሰረት አንደኛው ትረካ ነው ተግባራዊ የሆነው። አንደኛ ትረካ፡ ከምድር ተንቀሳቃሽ እንስሳት ሁሉ፤ ከወፍና ከነፍሳት ሁሉ፤ ንፁሕ የሆኑም ያልሆኑትም እንሰሳት፤ ሁለት ሁለት ሴት እና ወንድ እየሆኑ ወደ መርከብ እንደገቡ ይገልፃል - ዘፍጥረት 7፡8-9። ከእያንዳንዱ የእንሰሳ አይነት አራት ማለት ነው? ወይስ ሁለት? ለነገሩ ሁለት ብቻ ቢሆን እንኳ ቀላል እንዳይመስላችሁ። በምድር ላይ 5 ሚሊዮን ያህል የነፍሳት አይነቶች እንዳሉ ይገመታል - ዝንብ፣ ንብ፣ በረሮ። ከእያንዳንዱ አይነት ሁለት ሁለት እየተመረጠ በአጠቃላይ 10 ሚሊዮን ያህል ነፍሳት ወደ መርከቡ ይገባሉ ማለት ነው። በባህር ወይም ውሃ ውስጥ የሚኖሩትን ትተን፣ ጥቃቅኖቹን ነፍሳትም ሳይቆጠሩ፤ ወደ 20 ሺ ገደማ የተለያዩ የምድር እንሰሳት አሉ - እንሽላሊት፣ ዝሆን፣ ግመል፣ ጥንቸል፣ ጊንጥ፣ አሞራ... ወዘተ። ሁለት ሁለት እየሆኑ በአጠቃላይ ወደ 40 ሺ እንሰሳት ወደ መርከቧ ይገባሉ። የእግር ኳስ ሜዳ በማታክል መርከብ ውስጥ ማለት ነው። በዚያ ላይ የምግብና የውሃ ስንቅ መያዝ እንደሚገባው ታዟል። የኖህ ቤተሰቦችና እንሰሳቱ ሁሉ ከመርከቧ የሚወጡት ከአስራ ሁለት ወራት በኋላ ነዋ። ለ8ቱ የኖህ ቤተሰቦች፣ በሺህ ለሚቆጠሩ እንሰሳት፤ በሚሊዮን ለሚቆጠር ነፍሳት... የአንድ አመት ቀለብና ውሃ ብዙ ነው። እንግዲህ፤ የነገሩን አስቸጋሪነት ሲታይ ነው፤ የኖህ ታሪክ በከፊል ምሳሌያዊ ትረካ መሆን አለበት የሚባለው። ለማንኛውም የጥፋት ውኃ ከ5 ወራት በኋላ መጉደል እንደጀመረ፣ የኖህ መርከብ በአራራት ተራሮች ላይ እንደተቀመጠች፣ በ10ኛው ወር የተራሮች ጫፍ እንደታየ የሚተርከው ዘፍጥረት፤ ኖር መስኮት ከፍቶ ቁራ እና እርግብ እንደሰደደ ያወሳል። እርግቧ የምታርፍበት ቦታ አጥታ ተመለሰች፤ ከሰባት ቀን በኋላ ሲልካት በአፏ የወይራ ቅጠል ይዛ መጣች። አዲስ የበቀለ ይሁን ለአስር ወራት በጎርፍ ተቀብሮ የነበረ ወይራ ይሁን ባይታወቅም፤ ቅጠሉ ለምለም ነው። እንደገና ከሰባት ቀን በኋላ ለሶስተኛ ጊዜ እርግባን ሰደዳት፤ ተመልሳ አልመጣችም። ከ10 ወር ተኩል በኋላ የመርከቧ ክዳን ተከፈተ። ኖህ ከመርከቡ የወረደው ደግሞ አስራ ሁለት ወር ከደፈነው በኋላ ነው። ለእግዚአብሔርም መስዋዕት አቀረበ።

የሰው ዘር በሙሉ ከኖር ሶስት ልጆች ከሴም፣ ከካም እና ከያፌት ትውልድ የሚመዘዝ ሆነ ማለት ነው። የግሪኮቹ ኖህ ዱካልዮን ይባላል። አምላከ አማልክት ዙውስ፤ በሰው ልጆች የክፋት መንገድ ተቆጥቶ፤ የውኃ ጥፋት አዘዘባቸው። ለዘጠኝ ቀንና ሌሊት ዶፍ ዝናብ ለቀቀባቸው። ዱካልዮን ግን የአማልክቱን ሕግ የሚያከብርና የእውነትን መንገድ (በጽድቅ መንገድ) ይከተል ነበር። በዚህም ምክንያት የሰው ልጅን ከሚያጠፋ የውኃ መጥለቅለቅ እንዲድን ከአምላክ ተነግሮት መርከብ ሰርቷል። ውኃው አለምን እያጥለቀለቀ ሰው እና እንስሳን ሁሉ እየገደለ ሸለቆውን ብቻ ሳይሆን ተራሮችንም ይውጣል። ኩካልዮን እና ሚስቱ ግን መርከባቸው ውስጥ ናቸው። ውኃው መርከቧን እያንሳፈፈ ፓርናሰስ ተራራ ላይ አሳረፋት። በዚህ መንገድ ከሚስቱ ጋር ከጥፋት ውኃ ያመለጠው ዱካልዮን፤ ለአምላክ ዙውስ መስዋዕት አቀረበ። ሦስት ልጆችንም ወለደ። የሰው ዘርም ከሶስቱም ልጆች የሚመዘዝ ነው። በህንድ የሰንስክሪት ሃይማኖታዊ ፅሁፎችም ስለ ውኃ ጥፋት ይተርካሉ። ምድርና ሰማይ ከተፈጠሩ ከብዙ ዘመናት በኋላ በሰዎች ክፉ ተግባር የተነሳ ፈጣሪ በውኃ ሊያጥለቀልቃት ቢወስንም፤ አንድ በፅድቅ መንገድ የሚኖር ነበር - ሳትያራታ የሚባል። ፈጣሪ አምላክም ወደ ሳትያራታ መጥቶ፣ በ7 ቀን ውስጥ የጥፋት ውኃ እንደሚመጣ ነገረው። ግን ላንተ መርከብ ሰርቼ እሰጥሃለሁ። እፀዋትን ሁሉ፣ ከእንሰሳትም ሴት እና ወንድ ጥንዶችን ሰብስበህ ወደ መርከባ ግባ። ከውሃ ጥፋትም ትድናለህ አለው። የባሕር ምንጮች ተከፈቱ፤ የዝናፍ ዶፍ ወረደ። ምድር ተጥለቀለች። ሳትያራታ እና በመርከቧ ውስጥ የገቡ እፀዋትና እንሰሳት ግን ከጥፋት ዳኑ። ዳትያራታም ለአምላክ መስዋእት አቀረበ። BIBLE MYTHS AND THEIR PARALLELS IN OTHER RELIGIONS (ገፅ 24 - 25)። በእርግጥ የሰንስክሪት ፅሁፎች እድሜ 2400 ገደማ እንደሆነ ምሁራን ይገልፃሉ። የባቢሎናዊያኑ ትረካ ግን የ4000 አመት እድሜ አለው። ከ4000 አመት በፊት የተፃፈው የአትናፒሽቲም ታሪክ ከኖህ ጋር እንደሚመሳሰል ለብዙዎች አከራካሪ አይደለም። የዛሬዋ ኢራቅ የያኔዋ ባቢሎን አለምን ካጥለቀለቀው የጎርፍ ጥፋት እንደ ኖህ የተረፈው ሰው አትናፒሽቲም ይባላል። ስለጎርፉ እና ስለ አትናፒሽቲም ታሪክ ተፅፎ የሚገኘው፤ ከጊልጋሜሽ ገድል ጋር ነው። የጊልጋሜሽ ገድል Gilgamesh Epic በመባል የሚታወቀውና በ12 ሸክላዎች ላይ ተፅፎ የተገኘው ትረካ፤ የንጉስ ጊልጋሜሽን ጀግንነት ይዘረዝራል። ከዚሁ ጋር ግን፤ በጥንት ዘመን የሰው ልጅን ከምድረ ገፅ የሚያጠፋ የውኃ መዓት ደርሶ እንደነበር ይተርካል። በእብራውያኑ የኖህ ታሪክ፤ የውኃ ጥፋት የመጣው ከአዳም በ10ኛው ትውልድ በኖህ ዘመን እንደሆነ ይገልፃል። የባቢሎናውያኑ ትረካ ደግሞ፤ በ10ኛው ስርወመንግስት የጥፋት ውኃ አጋጥሞ፤ ኡትናቢሽቲም ብቻ እንደተረፈ ይገልፃል። አምላክ ባዘዘው መሰረት መርከብ ሰርቶ ከሁሉም የእንሰሳት አይነቶችም ሰብስቦ መርከቡ ውስጥ ገባ። በስድስት ቀን ዶፍ ዝናብ አለም ተጥለቀለቀች። መርከቧ ተንሳፍፋ ናሲር ተራራ ላይ አረፈች። በመጨረሻ ዝናቡ ሲቆም፤ ውሃው መጉደሉና አለመጉደሉን ለማወቅ እርግብ ሰደደ። በመጨረሻም ከነሚስቱ ከመርከቧ ወርዶ ለአምላክ መስዋእት አቀረበ። THE EPIC OF GILGAMESH፣ PENGUIN BOOKS 1999፣ ከገፅ 88 -100

 የጎፋ ቅ/ገብርኤል ምእመናን በደብሩ አስተዳዳሪ ተማረዋል

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስትያን መንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ‹‹መሠረተቢስ መረጃዎችን በማስተላለፍ ሕዝቡን ለማደናገር ይሠራሉ›› ባላቸው የሚዲያ ተቋማት ላይ ክስ መመሥረቱን አስታወቀ። በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሕዝብ ግንኙነት መምሪያ በወጣው ደብዳቤ እንደተገለጸው÷ ክሥ የተመሠረተባቸው አራቱ የሚዲያ ተቋማት÷ የኛ ፕሬስ ጋዜጣ፣ አርሒቡ፣ ሊያ እና ሎሚ የተባሉ መጽሔቶት ናቸው፡፡
የቅዱስ ፓትርያሪኩን ዜና ዕረፍት ተከትሎ ያለውን የሽግግር ወቅት በሰላማዊ መንገድ ለማከናወን ቅ/ሲኖዶስ በአንድነትና በመደማመጥ መንፈስ በተለያዩ ጊዜያት ጉባኤያትን በማድረግ፣በውጭም በውስጥም ያለውን ተጨባጭ ኹኔታ በመዳሰስና በሐቅ ላይ በመመርኮዝ የስድስተኛውን ፓትርያርክ ምርጫ ለማካሄድ ተግባራዊ እንቅስቃሴ በማድረግ ላይ መኾኑን መምሪያው ገልጾ÷ ‹‹አንዳንድ የነጻው ፕሬስ አባላት ሓላፊነት በጎደለው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ የሚመራውን የቅ/ሲኖዶስ ጉባኤ ውሎ በማብጠልጠልና በመተቸት የሚያወጧቸው ዘገባዎች በእጅጉ አሳዛኝና ቤተ ክርስቲያኒቱን ኾነ ብለው ለመበጥበጥ የተነሡ ያስመስላል›› ብሏል፡፡
በሕዝብ ግንኙነት መምሪያው ደብዳቤ እንደተመለከተው፣ በስም የተጠቀሱት ፕሬሶች በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትም ኾነ በሚመለከታቸው አካላት ማብራሪያና መግለጫ ያልተሰጠበትን ዜና ‹‹ከልዩ ልዩ የመረጃ መረቦች አግኝተናል›› በሚል ሽፋን ጽፈዋል፡፡ መምሪያው ‹‹በአባቶች መካከል ጠብና ችግር አለ ብሎ አንባቢው እንዲያምን ለማድረግ የሚጻፉ ናቸው›› ያላቸው እኒህ ጽሑፎች፣‹‹መሠረተቢስ አሉባልታዎች ብቻ ሳይሆኑ ቤተ ክርስቲያኒቱን የማፈራረስና ቅ/ሲኖዶሱን የመበታተን ዓላማ ያነገቡ ናቸው፡፡››
በመኾኑም በስም በተጠቀሱት አራት የፕሬስ ውጤቶች ላይ ቤተ ክርስቲያኒቱ ክሥ መመሥረቷንና ሕግና ሥርዐቱ በሚፈቅደው መሠረት ጉዳዩን በመከታተል የሕግ እርምት እንዲወሰድ በመንቀሳቀስ ላይ መኾኗ ተመልክቷል። ትክክለኛ መረጃን ለሕዝቡ ለማድረስ የሚመለከታቸውን አካላት በማነጋገር እውነተኛውን ዜና የሚያስተላልፉ የግል ሚዲያ ተቋማትን ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደምታደንቅና እንደምታመሰግን በደብዳቤው የገለጸው መምሪያው፣ በሚመለከተው የቤተ ክርስቲያኒቱ አካል መግለጫ ያልተሰጠባቸው ዘገባዎች ሁሉ ‹‹የሽግግር ወቅቱ በሰላማዊ መንገድ እንዳይከናወን የሚጥሩ ሰዎች የሚያናፍሱት የሐሰት ወሬ›› መኾኑን ሕዝቡ እንዲያውቀው ጠይቋል፡፡
በሌላ በኩል በአሁኑ ወቅት በቤተ ክህነቱ የተለያዩ ደረጃዎች የሚታዩ አስተዳደራዊ ችግሮች እየተባባሱ መኾናቸው፣ በየጊዜው ለአዲስ አድማስ ዝግጅት ክፍል እየደረሱ ያሉ የካህናትና ምእመናን አቤቱታዎች ያስረዳሉ፡፡ በተደጋጋሚ የዘገብነው በሰሜን ወሎ ሀ/ስብከት የቅ/ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም አስተዳደራዊ ችግር ዋነኛ ማሳያ ሲሆን በአስተዳደሩ ላይ ሲነሣ የቆየውና የከተማውን አስተዳደር ጨምሮ በመንግሥትና በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ከፍተኛ አካላት ዘንድ ሳይቀር በሚገባ የሚታወቀው የካህናቱና ምእመናኑ ጥያቄ በተለያዩ አጋጣሚዎች መመሪያ እንደተሰጠበት ቢነገርም እስከ አሁን በተጨባጭ ምላሽ እንዳላገኘ ነው የተዘገበው፡፡
ለመልካም አስተዳደር እንዲያመች በሚል በጥቅምቱ የቅ/ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ ውሳኔ÷ ለአራት በተከፈለው በአዲስ አበባ አህጉረ ስብከት ሥር በሚገኙ አንዳንድ አድባራትም ከሙስናና ብልሹ አሠራር ጋራ ተያይዘው በካህናቱና ምእመናኑ የሚነሡ በርካታ ጥያቄዎች እንዳሉ ለዝግጅት ክፍሉ የሚደርሱ መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡ በደቡብ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት የጎፋ መካነ ሕያዋን ቅ/ገብርኤል ካቴድራል÷ በካቴድራሉ አስተዳዳሪ ከእርሳቸውም ጋር በጸሐፊነት፣ በሒሳብ ሹምነት እና በገንዘብ ያዥነት በሚሠሩ የአስተዳደሩ ሠራተኞች ላይ ካለፈው ዓመት መጨረሻ ጀምሮ የሚነሡትና ከሀ/ስብከቱ ጽ/ቤት ባሻገር የመንበረ ፓትርያሪክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤቱ ጭምር እንደሚያውቀው የተነገረው አንድ የችግሩ አብነት ነው፡፡
በካቴድራሉ ሰንበት ት/ቤት እንደሚያገለግሉ የገለጹት ምእመናኑ ለዝግጅት ክፍላችን በሲዲና በሰነድ ያደረሷቸው መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፣ በክብረ በዓላትና በተለያዩ ጊዜያት ደብሩ በመባዕና በስእለት ለሚያገኘው ገንዘብና ንብረት ቆጠራ የሚካሄደው ግልጽነትንና ተጠያቂነትን የሚያሰፍነውን መመሪያ በመከተል ሳይሆን በአስተዳዳሪው ቀራቢዎች ነው፤የካቴድራሉ ገንዘብና ንብረት በትክክለኛ ሞዴላ ሞዴሎች ገቢ አይደረጉም፡፡ ከካቴድራሉ የንዋያተ ቅድሳት መሸጫና ሱቁ በተጓዳኝ ከሚሠራቸው የጨረታና የጉዞ አገልግሎቶች የሚሰበሰበው ገቢ በአግባቡ አይታወቅም፡፡
ሁለተኛውን ፓትርያሪክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስን ለመዘከር በተሠራው የአንደኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ከሚማሩ ተማሪዎች ክፍያ በሁለት ደረሰኞች የሚሰበሰብ ሲኾን አንዱ ደረሰኝ በካቴድራሉ ሰበካ ጉባኤም ሆነ በሀ/ስብከቱ አይታወቅም፡፡ ከፍለው ለመማር አቅም የሌላቸውን ተማሪዎች በበጎ አድራጊዎች ስፖንሰርሽፕ ለመደገፍ አስተዳደሩ የሚከተለው አሠራር ለምዝበራ የተጋለጠ በመኾኑ በችግረኛ ተማሪዎች ስም እየተነገደ ነው፡፡
በካቴድራሉ ደጃፍ መንግሥት በሰጠው ፈቃድ በካቴድራሉ ወጪ የሚሠራው የዝክረ ቴዎፍሎስ ዐደባባይ ሦስተኛ ዓመቱን ቢያስቆጥርም በየጊዜው ኾነ ተብሎ ዲዛይኑንና ጥራቱ ጠብቆ እንዳይሠራ እየተደረገ ግንባታው እየተጓተተ ነው፡፡ በግንባታው ሰበብ የሚገዙ የግንባታ ማቴሪያሎችና በቃል ኪዳን ሰነድ የተሰበሰበው ገንዘብ የግለሰቦች መኖሪያ ቤት መሥሪያና የግል ኑሮን ማበልጸጊያ እንደኾነ በምሬት የሚናገሩት ምእመናኑ÷ በቀድሞው አስተዳደር በአግባቡ ተጠብቆ የቆየው የካቴድራሉ ሕንጻ ቤተ መቅደስና የቅጽረ ቤተ ክርስቲያኑ ገጽታ በወቅቱ አስተዳደር ትኩረት የተነፈገው በመኾኑ በከፍተኛ ደረጃ መጎሳቆሉን፣ በአንጻሩ በካቴድራሉ ይዞታዎች በቤተ ክርስቲያን ቅጽር መገኘት የማይገባቸው ግለሰቦች ከአስተዳደሩ ጋራ በፈጠሩት የጥቅም ትስስር ለቤተ ክርስቲያን ቅድስናና ክብር ተቃራኒ የኾኑ ንግዳዊ ሥራዎችን (የከሰል፣ የአጠና ሽያጭና የአሳማ ርባታ) እንደሚያካሂዱ የሚናገሩት በከፍተኛ የሐዘን ስሜት ተውጠው ነው፡፡
ምእመናኑ በሰነድና በቃል ማብራሪያ አስደግፈው በካቴድራሉ አስተዳደር ላይ የሚያሰሟቸው አቤቱታዎች÷ የሰበካ ጉባኤ ቃለ ዐዋዲን፣ የቀኖና ቤተ ክርስቲያንንና የክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ጥሰትን የተመለከቱ ተጨማሪ አቤቱታዎችን ያካተተ ሲሆን ካለፈው ዓመት ሐምሌ ወር ጀምሮ ለመፍትሔው እንቅስቃሴ ሲደረግባቸው መቆየቱ ተገልጧል፡፡ አቤቱታዎቹ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በሠየመው አጥኚ ኮሚቴ በሚጣሩበት ወቅት የካቴድራሉ አስተዳደር ያመነባቸው ከመኾኑም በላይ ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ ለአምስት ዓመታት በአስተዳዳሪነት የቆዩት ቆሞስ አባ ኀይለ መለኰት ይኄይስ ከሓላፊነት ተነሥተው ለካቴድራሉ መንፈሳዊ አገልግሎትና የልማት አቅም በሚመጥን አለቃ እንዲተኩ ተወስኖ እንደነበር ምእመናኑ ያስታውሳሉ፡፡
ውሳኔውን በአግባቡ ተፈጻሚ በማድረግ መፍትሔ እንዲሰጣቸው በጥቅምት መጨረሻና በጥር መጀመሪያ ላይ ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ ጽ/ቤትና ለቅ/ሲኖዶስ ጽ/ቤት ጥያቄዎቻቸውን በተደራጀ አኳኋንና በሰላማዊ መንገድ እያቀረቡ እንደሚገኙ ምእመናኑ ገልጸው÷ የካቴድራሉ አስተዳደር ግን ይባስ ብሎ ‹‹አቤቱታ አቅራቢዎችን ተባብረዋል›› በሚል ዐሥር የካቴድራሉን ካህናት ከደመወዝና ከሥራ ማገዱን፣በካቴድራሉ ይዞታ ከሚገኘው መኖሪያ ቤቶቻቸውም እንዲለቁ ማዘዙን፣ ካቴድራሉ የሚገባውን ብቁ አስተዳደር እንዲያገኝ በሥርዐት የሚንቀሳቀሰውን የሰንበት ት/ቤት አመራርም በዐመፀኝነትና በፖለቲከኝነት በመወንጀል ከፍተኛ ጫና እየፈጠሩበት መኾኑን አስረድተዋል፡፡ በሓላፊነት ላይ የሚገኙት የካቴድራሉ አስተዳዳሪ ከሥልጣናቸው መነሣት ብቻ ሳይሆን የሕዝብን ሀብት ለብክነትና ለምዝበራ በመዳረጋቸው በሕግ መጠየቅ እንዳለባቸው የሚከራከሩት አቤቱታ አቅራቢዎቹ፣ በሕግ አገባብ ለሚመለከተው የፍትሕ አካል አስፈላጊውን ማስረጃ ለማቅረብ ዝግጅታቸውን ማጠናቀቃቸውን አስታውቀዋል፡፡


አሳ ሁልጊዜ በመረብ ብቻ አይጠመድም፡፡ የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራሙ እንዲህ ያለ አሳዛኝ ውጤት በማስመዝገብ ሲከሸፍ፣ ብዙዎቹ ቤተእስራኤሎችና እነሱን ለመርዳት ተብለው የተቋቋሙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የእስራኤል መንግስት ቤተእስራእሎችን ለማዋሀድ በሚል የቀረፃቸውን ሌሎች ፕሮግራሞች የአፈፃፀማቸውን ጉዳይ መለስ ብሎ ለመገምገም አረፍ የሚልበት ታዛና የጥሞና ጊዜ ያገኛል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር፡፡

በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኙ የድሩዝ ማህበረሠብ አባላት ተለይተው ከሚታወቁበት ነገሮች አንዱ ለሚኖሩበት ሀገር መንግስት ያላቸው የማያወላውል ታማኝነት ነው፡፡ በድፍን የመካከለኛው ምስራቅ ሀገራት ውስጥ በሀገሬ የሚኖሩ ድሩዞች የተቃውሞ ድምፃቸውን አሠሙብኝ ወይም ደግሞ በአመጽ ተነሱብኝ ብሎ ስሞታውን ያሠማም ሆነ የሚያሠማ መንግስት ለመድሀኒትም ቢሆን ተፈልጐ አይገኝም፡፡ በ1970ና 80ዎቹ የሊባኖስ የእርስ በርስ ጦርነት ወቅት የራሳቸውን ሚሊሻ በማቋቋም ነፍጥ አንስተው ውጊያ የገጠሙት ህልውናቸዉን አደጋ ላይ ከጣሉት ታጣቂ የሚሊሻ ቡድኖች ጋር እንጂ ከሊባኖስ መንግስት ወታደሮች ጋር አልነበረም፡፡ ቤተእስራኤሎችም በእስራኤል የሚኖሩ “ድሩዞች” አይነት ነበሩ፡፡

እግራቸዉ የእስራኤልን መሬት ገና ከመርገጡ ጀምሮ የሂብሩ ጋዜጦች መብታቸውንና ነፃነታቸውን የሚጋፋ፣ ሠብአዊ ክብራቸዉንም የሚያንቋሽሽ አስከፊ የጥላቻ ዘመቻ ሲከፍቱባቸው፤ ያይጥ ምስክር ድንቢጥ እንዲሉ ጋዜጦችንም ተከትለው የተለያዩ የእስራኤል ተቋማት፣ የተለያዩ የእስራኤል የመንግስት ባለስልጣናት፣ የሀይማኖት መሪዎችና የማህበረሠብ አባላት ተዘርዝሮ የማያልቅ የዘረኝነት በደል ሲፈጽሙባቸው በእስራኤል መንግስት ላይ የነበራቸው ተስፋና እምነት እንደተጠበቀ ነበር፡፡ ቤተእስራኤሎቹ ለእስራኤል መንግስት የነበራቸውን ክብርና እምነት እንዲህ በቀላሉ እሰየው ብለው ለድርድር የሚያቀርቡት ጉዳይ ጨርሶ አልነበረም፡፡ የተስፋዋ ሀገራችን በሚሏት እስራኤል ይሆናል፤ ያጋጥመናልም ብለው ጨርሰው ባልገመቱት ሁኔታ ያ ሁሉ ግፍና በደል ወደው እስኪጠሉ ድረስ ሲፈራረቅባቸው የእስራኤል መንግስት በወቅቱ የሠጣቸዉ መልስ አልነበረም፡፡ በዘርና በቀለማቸው የተነሳም ኢትዮጵያ ውስጥ ይኖሩ በነበረበት ጊዜ እንኳ ማንም ብሏቸው ወይም ጠርቷቸው የማያውቀውን “ኩሽም” (ባሪያ) የሚል መዘባበቻ ሲሆኑ የእስራኤል መንግስት ግን ተፈልጐም እንኳ ሊገኝ አልቻለም ነበር፡፡ ይህ ሁሉ ሆኖ ግን ቤተእስራኤላውያን ከተጣዱበት የዘረኝነት መጥበሻ ላይ እንዳሉ በፀጥታ መገላበጥን እንጂ በሚያምኑትና በሚያከብሩት የእስራኤል መንግስት ላይ ልባቸውን ለማሻከርም ሆነ ፊታቸውን ለማጥቆር ጨርሶ አልሞከሩም፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ በዚያን ወቅት በእስራኤል መንግስት ላይ ይህን ለማድረግ የሚያስችል አንጀት አልነበራቸውም ነበር፡፡

እንደ እስራኤል ድሩዞች ተደርገው መቆጠር ጀምረው የነበሩት ቤተእስራኤሎች ማንም ሊያደርጉት ይችላሉ ብሎ ባልገመተው ሁኔታ በእስራኤል መንግስት ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ በተቃውሞ አደባባይ በመውጣት የእየሩሳሌምንና የሌሎችም የእስራኤል ታላላቅ ከተሞች ለአንድ ወር በዘለቀ ጠንካራ የተቃውም ስብሠባና ሠልፍ ቀውጢ ያደረጉት ሀይማኖታቸውን በተመለከተ በከፍተኛ ሀፍረት ላይ የጣላቸውና በእጅጉ ያሸማቀቃቸው በደል ከደረሠባቸው በኋላ ነበር፡፡ ቤተእስራኤሎች ከዚህ በፊት በከፍተኛ ትዕግስትና ሆደ ሠፊነት ይዘዋቸው የነበሩት የተለያዩ ፈርጀ ብዙ ችግሮች ሁነኛ መፍትሄ እንዲያገኙ የእስራኤል መንግስትን ሳያሠልሱ መወትወት የጀመሩትና አልፎ አልፎም የተቃውሞ ድምፃቸውን ማሠማት የጀመሩትም ከዚህ ጊዜ በኋላ ነው፡፡ የእስራኤል መንግስት ግን የቤተእስራኤሎችን ችግር የተረዳው ገልብጦ በተቃራኒው ነበር፡፡ ለእስራኤል መንግስት የቤተእስራኤሎች ችግር እውነተኛ ችግር ሳይሆን እነሱን ለማዋሀድ በሚል የሚያደረግላቸው መጠነ ሠፊ እርዳታ ስለበዛባቸው ከመቅበጣቸው የተነሳ የመጣ ችግር አድርጐ ነበር፡፡ እናም በየጊዜው የሚያቀርቡትን የመፍትሄ አቤቱታ ለማዳመጥ የሚያስችል ጊዜውም ሆነ ልቦናና የመስሚያ ጆሮ አልነበረውም፡፡

ይልቁንስ ነገሩ ሁሉ የምግብ ፍላጐት ከመብላት ጋር ይመጣና ይጨምራል እንደሚባለው ሆኖበት ነበር፡፡ እናም አንዱ ጥፋት በጊዜ የመታረም እድል ማግኘት ሳይችል በሌላኛው ላይ እየተደራረበ ሄዶ፣ ቤተእስራኤሎቹን ከተቀረው የእስራኤል ማህበረሠብ ጋር በሚገባ ለማዋሀድ በሚል በእስራኤል መንግስት ተደግሶ የነበረውን “የቅልቅሉን” ድግስ የተጠሩት እንግዶች ሊቀምሱት እንዳይችሉ አድርጐ በአሳዛኝ ሁኔታ እንጀራውን አሻገተው፣ ወጡን እጅ እጅ እንዲል አደረገው፡፡ የእስራኤል መንግስት ቤተእስራኤሎች የራሳቸውን ቤት መግዛት እንዲችሉ ለማበረታታት በሚል በሠጣቸው ብድር አማካኝነት እስከዛሬ አስር አመት ድረስ አስር ሺ አምስት መቶ የሚሆኑ ቤተእስራኤላውያን አብዛኞቹ ባለ አንድ መኝታ ቤት የሆኑ አፓርታማዎችን ወይም የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ለመግዛት ችለዋል፡፡ ከተቀሩት ውስጥ አብዛኞቹ በመንግስት የኪራይ ቤቶች ውስጥ ሲኖሩ፣ ከዛሬ አስር አመት ወዲህ ወደ እስራኤል የመጡት ደግሞ ዛሬም ድረስ በመጠለያ ጣቢያዎችና በተንቀሳቃሽ ቤቶች ውስጥ ይኖራሉ፡፡ ለቤተእስራኤሎች ተዘርግቶ የነበረው የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራም እንደተገለፀው የተወሰኑትን የቤት ባለቤት ሊያደርጋቸው ቢችልም የሚፈለገውንና ቀድሞውኑ የታሠበለትን ውጤት ሳያመጣ እንደከሸፈ በእስራኤል ክኔሴት (ፓርላማ) ተመስክሮበታል፡፡ ለዚህ ደግሞ ከእስራኤል መንግስት ሌላ በተጠያቂነት ቀርቦ ቃሉን ሊሠጥ የሚችል ተጠያቂ አካል ሊኖር አይችልም፡፡ እንዴት ቢባል… የእስራኤል መንግስት ይህን የብድር ፕሮግራም የጀመርኩት ቤተእስራኤሎችን ለመርዳት በሚል “ቅን” መንፈስ ነው በማለት ሞቅ ያለ ፕሮፓጋንዳውን ቢለቅም ለፕሮግራሙ አፈፃፀም ሙሉ ቀልቡንና ልቡን ጨርሶ አልሠጠም ነበር፡፡ ፕሮግራሙን ለማስፈፀም የተጠቀመባቸው ስትራተጂዎች በሙሉ የተንጋደዱና አቅም ባላቸው ባለሙያዎች የተያዙና የተመሩ ጨርሶ አልነበሩም፡፡ የፕሮግራሙ ጠቅላላ አሠራርም የግብር ይውጣ ነበር፡፡

ይህን የብድር ፕሮግራም አሠራር በትኩረት በመከታተል አፈፃፀሙን በደንብ መገምገም የቻሉ የማህበራዊ ኑሮ ጥናት ባለሙያዎች፤ የእስራኤል መንግስት ቀድሞውን ቢሆን የእስራኤል “ኩሽም” የሆኑትን ቤተእስራኤሎች ከተቀረው “ናሽም” (ነጭ) የእስራኤል ማህበረሠብ ተለይተው በአንድ አካባቢ ብቻ ተከማችተው እንዲኖሩ ለማድረግ እጅግ በረቀቀ መንገድ ነድፎ ያዘጋጀው ፕሮግራም ነው እያሉ በሰላ ትችት ሲያብጠለጥሉት ኖረዋል፡፡ ይህን የባለሙያዎች ትችት ትክክል ነውም አይደለምም ብሎ መከራከሩ አጨቃጫቂ ሊሆን ይችላል፡፡ የሆኖ ሆኖ ግን የእስራኤል መንግስት በፈለገው አይነት አላማ ቢያዘጋጅም የመጨረሻው ውጤቱ ግን ከቀረበው ትችት ጋር አንድ አይነት ነበር፡፡ የመኖሪያ ቤት ለመግዛት ብድር የወሰዱ ቤተእስራኤሎች አብዛኞቹ ስራ አጥ ነበሩ፡፡ ስራ አላቸው የሚባሉትም ቢሆን እጅግ ዝቅተኛ ክፍያ በሚያስገኙ የስራ መስኮች ላይ የተሰማሩ ነበሩ፡፡ እናም ከወሰዱት ብድር ላይ ትንሽ ጨምረው በተሻሉና መካከለኛ ገቢ አላቸው ወደሚባሉትና ሁሉም አይነት የመሠረተ ልማት አገልግሎቶች በተሟሉባቸው አካባቢዎች ውስጥ ቤት ለመግዛት የሚችሉ አልነበሩም፡፡ ሁሉም በብድር ያገኙትን ገንዘብ ይዘው ያመሩት ርካሽ የመኖሪያ ቤቶች ወደሚሸጡባቸው፣ ምንም አይነት የመሠረተ ልማት አገልግሎቶች ባልተዘረጉባቸው ኋላቀርና ጭራሹኑ ወደተዘነጉት አካባቢዎች ነበር፡፡ ይህም ሁኔታ በድህነት የተቆራመዱ፣ በጨለማ የተዋጡና፣

ከሌላው የእስራኤል ህብረተሠብ በእጅጉ የተጉላሉ “የኩሽም ቤተእስራኤሎች” የመኖሪያ ጌቶዎች እንዲመሠረቱ ዋነኛ ምክንያት ለመሆን በቃ፡፡ የማታ ማታ አፍላ፣ ኪርያት ጋት፣ ኦር ይሁዳ፣ ኪርያት ማላኪህና የመሳሠሉት በተለያዩ የእስራኤል ከተሞች ውስጥ የሚገኙ ሠፈሮች “ናሽም” እስራኤላውያን ዝር የማይሉባቸዉ ወይም ዝር ሊሉባቸው በጣም የሚፈሯቸው የቤተእስራኤሎች መኖሪያ ጌቶ ሠፈሮች በመሆን አለም አቀፍ እውቅናን ለመጐናፀፍ ቻሉ፡፡ አሳ ሁልጊዜ በመረብ ብቻ አይጠመድም፡፡ የመኖሪያ ቤት ግዢ የብድር ፕሮግራሙ እንዲህ ያለ አሳዛኝ ውጤት በማስመዝገብ ሲከሸፍ፣ ብዙዎቹ ቤተእስራኤሎችና እነሱን ለመርዳት ተብለው የተቋቋሙ መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የእስራኤል መንግስት ቤተእስራእሎችን ለማዋሀድ በሚል የቀረፃቸውን ሌሎች ፕሮግራሞች የአፈፃፀማቸውን ጉዳይ መለስ ብሎ ለመገምገም አረፍ የሚልበት ታዛና የጥሞና ጊዜ ያገኛል ብለው ተስፋ አድርገው ነበር፡፡ ይህንን ተስፋ ያደረጉትም “አንዴ የተሸነፈ ሁለት ጊዜ ያፍራል” የሚለው እድሜ ጠገብ የማስተዋልና የብልሀት አነጋገር መቼም ቢሆን ለእስራኤል መንግስት አይጠፋውም ከሚል ግምታቸው በመነሳት ነበር፡፡ ቶማስ ሐንዴ የተባለ ደራሲ “Mr. Nicholas” በሚል ርዕስ በ1952 ዓ.ም ባሳተመው መጽሀፍ፤ አደጋን ለመጋፈጥ የማይፈልጉ ቦቅቧቃ ሰዎች፤ ምንም ቢያደርጉ ምን በአስደናቂ ነገሮች የተሞላ ህይወት ለመኖርና አስደናቂ ውጤቶችን ለመቀዳጀት ከቶውንም አይችሉም ይላል፡፡ ይህ የቶማስ ሒንዴ አባባል በቀላልና አጭር አገላለጽ ሲቀመጥ “ጀብዱ ለጀብደኞች፣ (Adventure is for fare adventurous) ማለት ነው፡፡ ከ1973 ዓ.ም የዬም ኪፑር ጦርነት ድል ማግስት ጀምሮ እስከአሁን ድረስ በወይዘሮ ጐልዳ ሜየርም ሆነ በቤንጃሚን ናታንያሁ ጠቅላይ ሚኒስትርነት የተመራው የእስራኤል መንግስት ወታደራዊ የሆነውን ነገር ለጊዜው ትተን ማህበራዊ ጉዳዮችን ብቻ በተመለከተ የወሠዳቸውን የተለያዩ የፖሊሲም ሆነ ሌሎች እርምጃዎችን በስሱ በመገምገም ብቻ የእስራኤል መንግስት ጀብዱ (Adventure) አድናቂና ጀብደኛ (Adventurous) መንግስት እንደሆነ ለመገንዘብ ምንም አይነት የአዕምሮ ብሩህነትን አይጠይቅም፡፡

አሳዛኙ ነገር ግን እነዚያ ቤተእስራኤሎችና የቤተእስራኤል ድርጅቶች ይህንን በወጉ መገንዘብ አለመቻላቸው አሊያም ጨርሰው መዘንጋታቸው ነበር፡፡ በዚህ የተነሳም የእስራኤል መንግስት፤ የመጀመሪያው ውሸት ወደ ሁለተኛው ውሸት ይመራል እንደሚባለው አይነት ከመጀመሪያው ስህተት ወደ ሁለተኛው ተሸጋገረ፡፡ የእስራኤል መንግስት ቤተእስራኤሎችን ለማዋሃድ በነደፈው ማስተር ፕላን፣ የስራ እድልን በተመለከተ ያስቀመጠው ዋነኛው ግቡ ለቤተእስራኤሎች የሙያና የክህሎት ስልጠና መስጠት የሚል ነው፡፡ በዚህ መሠረት የእስራኤል የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ለቤተእስራኤሎቹ በቂያቸው ነው ብሎ የመረጠላቸው የሙያና የክህሎት የስልጠና መስኮች የብረታብረት፣ የእንጨት ስራ፣ የነርሲንግ፣ የሆቴል መስተንግዶና፣ የልብስ ስፌት ናቸው፡፡ የእውነት ለመናገር ባለእጅነትን አምላክ ሁልጊዜ ለቤተእስራኤሎች ብሎ የጣፈው ሙያ ይመስላል፡፡ ይህ ላይ ላዩን ሲያዩት አሪፍ ነገር ይመስላል፡፡ ነገር ግን ቤተእስራኤሎች አስቀድሞ በተመረጠላቸውና በተወሰነባቸው በእነዚህ የስልጠና መስኮች የሙያ ስልጠና እንዲወስዱ ዝግጅት እየተደረገ ባለበት ወቅትም ሆነ ከዚያ ቀደም ብሎ እነዚህ የስራ መስኮች በፍልስጤማውያንና በሌሎች ዜጐች ከአፍ እስከደገፋቸው ተይዘው ነበር፡፡ እናም ቤተእስራኤሎቹ እንደታሰበው ሰልጥነው ቢወጡም፣ በእስራኤል የስራ እድል መድረክ ላይ ተወዳድረው ስራ ማግኘት በእጅጉ አዳጋች ሆነባቸው፡፡ በመጨረሻም ያተረፉት ነገር የእስራኤልን አውራጐዳናዎች ማጽዳት፣ መናኛ ስራዎችን እጅግ መናኛ በሆነ ክፍያ መስራትና የእስራኤል የአዲስ መጤዎችና የውህደት ሚኒስቴር የሁልጊዜም የእርዳታ ጥገኛ ሆኖ መቅረትን ነበር፡፡ በትምህርትና በሌሎች የማህበራዊ ዘርፎች የተገኘው ውጤትም ከዚህ ጨርሶ የተለየ አልነበረም፡፡ ቤተእስራኤላውያን በተሻለ ተዋህደውበታል ተብሎ ሊጠቀስ የሚችለው ተቋም ቢኖር የእስራኤል የጦር ሀይል ብቻ ነው፡፡

ቤተእስራኤሎች እውነተኛ እስራኤላዊ መሆናቸውንና ለእስራኤል ያላቸውን ፍቅርና ታማኝነት የህይወት መስዋዕትነትም ቢሆን በመክፈል ለማሳየት ቁርጠኛ አላማ የያዘና ለዚህም የምራቸውን የተዘጋጁ ነበሩ፡፡ የእስራኤል የመከላከያ ሠራዊትን በገፍ የተቀላቀሉትም በዚህ የተነሳ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ ተቋምም ቢሆን ያጋጠማቸው የዘረኝነት መድልዎ እንዲህ በቀላሉ ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም፡፡ የእስራኤል መንግስት ችግሮቹን በጊዜ ለመፍታት ባለመቻሉ ሳይሆን ፈጽሞ ባለመፈለጉ የተነሳ በሁሉም ነገር የመጨረሻውን ዝቃጭ ደረጃ የያዘ አንድ የእስራኤል ማህበረሠብ ለመፍጠር ቻለ፡፡ ቤተእስራኤሎችም የማታ ማታ ከመላው የእስራኤል ማህበረሠብ ተለይተው የዘረኝነት ጥቃትና መድልዎ ሰለባ ሆነውና የመጨረሻውን ዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ይዘው ራሳቸውን አገኙት፡፡ ይህም ሁኔታ የአብዛኞቹን ቤተእስራኤሎች ቤተሠብ ክፉኛ አመሠቃቀለው፡፡ በእድሜ የገፉት ለከፍተኛ ግራ መጋባት ሲዳረጉ፣ ወጣቶቹ ደግሞ በከፍተኛ የማንነት ቀውስ ውስጥ በመውደቃቸው “ራስታ” ለመሆን ባዘኑ፡፡ እነዚሁ ቤተእስራኤሎች በከፍተኛ የተስፋ መቁረጥ ስሜት ውስጥ ስለወደቁ፣ በወንጀል ድርጊት መሳተፍ፣ የወንጀል ቡድን አባል መሆን፣ አደንዛዥ እጽ መጠቀምና ማዘዋወር ድርጊት ውስጥ መሳተፍ ጀመሩ፡፡

በዚህም የተነሳ የቤተእስራኤል ወጣቶች የእስራኤልን እስር ቤቶች ማጨናነቅ ተያያዙት፡፡ ለህይወት ጉጉት ማጣታቸውና ከህይወት ትግል ማፈግፈጋቸውም መገዳደልንና ራስን ማጥፋትን እንደ ዋነኛ የችግር መገላገያ መፍትሄ አድርገው ይቆጥሩት ጀመር፡፡ የተቀረው የእስራኤል ህዝብ በአባታቸው ኖህ እንደተባረኩት ልጆች እንደ ሴምና ያፌት ናቸው፡፡ ማርና ወተቱን እለት ተዕለት እየተቆጣጠረ የቆዳ ስልቻቸውን የሚሞላላቸው የራሳቸው አሳላፊ አላቸው፡፡ የቤተእስራኤሎች ኩባያ ግን ባዶ ነው፡፡ ምክንያቱም ከሀገሪቱ የማርና የወተት ሠልፍ የእነሱ ተራ ከሁሉም የመጨረሻው ስለሆነ ነው፡፡ አሁን እነሱ ለአምላካቸው እያቀረቡት ያለው ፀሎት አንድ ብቻ ነው፡፡ አምላካቸው የራሳቸውን ነህምያ (ነቢይ) እንዲሠጣቸው!! አሜን ያድርግላቸው!

መልክአ፣ ኢትዮጵያ ፪

አሁንም ከአትላንታ ጆርጅያ አልወጣኹም፡፡ ባለፈው ሣምንት ጽሑፌን ለዛሬ ያቆየኹት በራቁት ዳንስ ቤት (Strip Club) ውስጥ በአግራሞት ስለተመለከትኋት ሐበሻዊ - መልክ - ራቁት - ደናሽ ልተርክላችኹ ቀጠሮ ይዤ ነበርና ከዚያው ልቀጥልላችኹ፡፡ ዓርብ እና ቅዳሜ የአሜሪካኖቹ የመዝናኛ ዕለታት ናቸው፡፡ ማታ ወጥቶ መዝናናት የሚያሰኘው ካለ ዓርብ እስኪመጣ መጠበቅ ግዴታው ነው፡፡ ከዚያ ውጭ ባሉት ቀናት ወደ ምሽት መዝናኛ ቤቶች ጐራ ማለት የብርዳም (ቁራጭ) ምሽቶች ሰለባ ያደርጋል። መዝናኛ ቤቶቹ ዐይነታቸው ለየቅል ነው። የአትላንታ ምሽት ቤቶችም እንደ ሌሎቹ የአሜሪካ ከተሞች ሁሉ ዓርብን መስለዋል። መኪና ማቆሚያዎች በተሽከርካሪዎች፣ መግቢያ በሮች ደግሞ በሰው ተጨናንቀዋል። በከተማው ይገኛሉ ሲባል ከሰማኋቸው ራቁት ዳንስ ቤቶች ሁሉ እኔ አሁን ያለሁበትን መርጫለኹ፡፡ ሐበሻዊ መልክ ያላት ደናሽ በዚህ ቤት ትገኛለችና፡፡ ቀናት በፈጀ ልመና ቦታውን ሊያስጐበኙኝ ፈቃደኛ ሆነው ያካሄዱኝ ሦስት ወንድ ጓደኞቼ ዓርብ እና ቅዳሜ ተመራጭ ቀናት መሆናቸውን በመጠቆም ይዘውኝ የወጡት በአንዱ ዓርብ ነው፡፡ ከቦታው ደረስን፡፡

ከፊት ለፊታችን በተንጣለለው የመኪና ማቆሚያ ላይ ስፍር ቁጥር የሌላቸው መኪኖች ተደርድረዋል። ዙሪያ ገባውን በተደረገ ፍለጋ እንደምንም አንድ ማቆሚያ ተገኘ፡፡ መኪናችንን ግራና ቀኙን ጠብቆ ያለምንም ስሕተት ለማቆም የሁሉም ሰው ርዳታ አስፈልጐ ነበር፡፡ ቀድመው ቦታ ይዘው በቆሙት መኪኖች ላይ ጭረት ማሳረፍ በቀላሉ የሚታለፍ ጥፋት አይደለም፡፡ በፊልም እና በማስታወቂያ የማውቃቸው የዓለም ውድ ሞዴል መኪኖች በመኪና ማቆሚያው ከተደረደሩት መካከል ቀላል የማይባለውን ቁጥር ይዘዋል፡፡ የቤቱ መለዮ የኾነው ማስታወቂያ ከሩቅ ይጣራል፡፡ በዐሥራ አምስት ደረጃዎች ከፍታ በተሠራ የቪላ ቤት ቅርጽ ግዙፍ ቤት አናት ላይ “Pink Pony” የሚል ማስታወቂያ ተለጥፎበታል፡፡ በታላላቅ ፊደላት የተቀረጸ ሲሆን ሮዝ መልክ ባለው መብራት ያሸበረቀ ነው፡፡ በሁለቱ ቃላት መካከል ፊቷን ያዞረች ራቁት ደናሽ ሴት ምስል ተጣምሮ ተሰቅሏል። ወደ መግቢያው ስንጠጋ ሁለት ሙሉ ጥቁር የፖሊስ ልብስ የለበሱ ነጭ ጠባቂዎች ዙሪያቸውን መሣሪያ ታጥቀው ወደ ዳንስ ቤቱ የሚገቡት ሰዎች ዕድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች አለመሆኑን መታወቂያ እያገላበጡ በማየት የይለፍ ምልክት ይሰጣሉ። ተራችንን ጠብቀን የይለፍ ማኅተሙን እጃችን ላይ ካስመታን በኋላ ተራ በተራ ፍተሻችንን እያጠናቀቅን የመግቢያ ክፍያ ወደሚከፈልበት ቦታ ሄድን፡፡

ለአንድ ሰው መግቢያ 15 ዶላር ይከፈል ነበርና ለአራታችን ለመክፈል ወደ ሒሳብ ተቀባዩዋ ስንጠጋ፣ ወደኋላ ቀርቶ የነበረው ታክሲ አሽከርካሪ ጓደኛችን ለሒሳብ ተቀባዩዋ የሆነ ምልክት አሳያት፤ የገባት አልመሰለኝም፤ ምን እንደሚል ደግማ ጠየቀችው፡፡ ባለታክሲ መሆኑንና ደንበኞችን ይዞ መምጣቱን ጠቆማት፡፡ “ገባኝ” በሚል ስሜት እየተፍለቀለቀች የኛን ወስዳ የሱን መለሰችልን፡፡ ኢትዮጵያውያን ባለታክሲዎች ደንበኛ ይዘው ወደዚህ ቤት ከመጡ መግቢያ ሳይከፍሉ ገብተው ይታደማሉ ወይም ደግሞ ኮሚሽን ይቀበላሉ፡፡ በአሜሪካ ከአምስት ኢትዮጵያውያን ጋር የመገናኘት ዕድል ቢገጥማችሁ አንዱ ባለታክሲ መሆኑ ግድ ነውና እዚህ ቤትም አብረውኝ ከመጡት ጓደኞቼ አንዱ ባለታክሲ ነው፡፡ እንዲህ ላለው የከተማ ወሬ ከእነሱ የቀረበ ስለማይኖር ጥያቄዬን ለሱው መወርወር ጀመርኹ፡፡ “የዳንስ ቤቱ ጠባቂዎች ይህን ሁሉ ሽጉጥ የታጠቁት ለምንድነው?” ስል ጠየቅኹት፡፡ “የትኞቹ? በር ላይ ያለፍናቸው ነው? ፖሊሶች ናቸዋ” አለኝ፡፡ እንደገና ወደኋላ ተመልሼ መታወቂያቸውን መጠየቅ አማረኝ። በራቁት ዳንስ ቤት መግቢያ በር ላይ ፖሊሶች ቆመው በትጋት ይቆጣጠራሉ። “ለዐቅመ አዳምና ሔዋን የደረሳችሁ እንደፍጥራጥራችሁ” በሚል ስሜት ወደ ውስጥ ያሳልፋሉ፡፡ የቆረጥነውን ትኬት ሁለተኛው በር ላይ ላገኘነው ተቆጣጣሪ ሰጥተን ወደ ውስጥ ዘለቅን፡፡ በሩ ወለል ብሎ ሲከፈት ድፍረቴ ጥሎኝ ጠፋ፡፡ ሰውነቴ በላብ ተዘፈቀ፡፡ ከወደፊት ይልቅ ወደኋላ የመመለስ ፍላጐቴ ጨመረ፡፡ የደም ግፊት እንዳለበት ሰው የጭንቅላቴን የኋለኛ ክፍል ጨምድዶ ያዘኝ። በድንጋጤ ክው ብዬ ቀረኹ፡፡ ወድጄ እና ፈቅጄ የመጣሁ ሳይሆን የሆነ ሰው በሲዖል ደጃፍ አምጥቶ የጣለኝ መሰለኝ፡፡

ዐይኔ ለጊዜው ማስተዋል የቻለው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ እጅግ ሰፊ በሆነው ዳንስ ቤት ውስጥ ርቃናቸውን የሆኑ በርካታ ሴቶች ይርመሰመሳሉ፡፡ ከዚህ ቀደም አዲስ አበባ ውስጥ በጐበኘኋቸው “ስም ያወጡ” ራቁት ዳንስ ቤቶች ውስጥ የተመለከትኋቸው ኢትዮጵያውያን እንስቶች “በስንት ጣዕማቸው?” አሰኘኝ፡፡ ጡታቸውን እና ሃፍረተ -ገላቸውን በእራፊ ጨርቅም ቢሆን ሸፈን ያደርጉታል፡፡ ያኔ ይህን ቢዝነስ ሠለጠኑ ከተባሉት አገሮች ቀድተው አዲስ አበባ ያመጡትን የዳንስ ቤት ባለቤቶች ረግሜያቸው ነበር፡፡ ዛሬ ግን ለእራፊ ጨርቃቸውም ቢሆን አመሰገንኋቸው፡፡ ያጋነንኹ ካልመሰላችሁ እውነቱን ልንገራችኹ፡፡ ከቆምኹበት ብንቀሳቀስ የምወድቅ ስለመሰለኝ አንገቴን ወደ መሬት ቀብሬ ትንሽ ትንፋሽ ወሰድኹ፡፡ ጐትቼ ያመጣኋቸው ወዳጆቼ ወኔ ሲከዳኝ ሲያዩኝ ተሣሣቁብኝ፡፡ ከፊል እርቃኗን የኾነች አስተናጋጅ ፊቷን እንደ ጸዳል አብርታ በሚያብረቀርቅ ፈገግታ “ቁጥራችሁን ንገሩኝና ቦታ ልስጣችሁ?” ስትል ጠየቀች። ባይሆን ከለል ያለ ቦታ እንዳለ ለማየት እንደምንም ተጣጥሬ ቀና አልኹ፡፡ የቤቱ ስፋት በአንድ ጊዜ ይህን ለመቃኘት አያስችልም፡፡ ቀና ማለቴ ከፈራኋቸው ራቁት ሰውነቶች ጋር መልሶ አገጣጠመኝ፡፡ “የቱ ጋር እንቀመጥ?” በሚል ጠያቂ አስተያየት ሁሉም ወደ እኔ ተመለከቱ “ያስመጣሽን አንቺ ነሽ፤ እንግዲህ ተወጪው ይመስልባቸዋል፡፡ ከለል ያለ ቦታ ካገኘን ብዬ ከእነድንጋጤዬ ጠየቅኋቸው፡፡

ባለታክሲው ወዳጄ “ለዚች ልብሽ ነው እንዴ?” ሲል በድንጋጤዬ ላይ አላገጠብኝ፡፡ በቤተኝነት ስሜትም ከቤቱ መግቢያ በር በስተቀኝ በኩል ካለው የመጠጥ መሸጫ ክብ ባንኮኒ ላይ እንድንቀመጥ ወደዚያው ወሰደን፡፡ በዙሪያ ገባው ምን እየተከናወነ እንደሆነ የማየት አቅም ለጊዜው ስላጣሁ ዐይኔን በክቡ ባንኮኒ ውስጥ ቆመው መጠጥ በሚሸጡት ሴት እና ወንዶች ላይ ተከልኹ፡፡ አማራጭ ማጣት ኾኖብኝ እንጂ እኒህም የሚታዩ ሆነው አልነበረም፡፡ አንዳንዶቹ በውስጥ ሱሪ እና በጡት ማስያዣያ፣ ከፊሎቹ አጭር ቁምጣ በተጣበቀ አላባሽ፣ ከሰውነታቸው ከፊሉን አራቁተው ለማሻሻጫነት የቆሙ ናቸው፡፡ የአዲስ አበቦቹን “ከፊል ራቁት ደናሾች” ከእራፊው ጨርቅ በመለስ ያለውን ገላቸውን አጋልጠው ለሽያጭ በማቅረብ በቀጫጭን ብረቶች ታግዘው፣ ሰውነታቸውን ከወሲብ ቀስቃሽ ሙዚቃ ጋር አዋሕደው እየተገለባበጡ የሽልማት ገንዘብ ሲሰበስቡ ሳይ “አይ ድህነት አያደርገው የለ” ስል ለእንስቶቹ ሆዴ ተላውሶላቸው ነበር፡፡ በርካቶች ሥራ ፍለጋ በሚሰደዱባት የዓለም ቁንጮ በሆነችው ሀገረ አሜሪካ፣ ገላቸውን ለሽያጭ ላቀረቡት ወጣት እንስቶችስ “አይ የእንጀራ ነገር” ስል ደረቴን ልድቃላቸው ይሆን? ጉዳዩ የእንጀራ አይመስልም፤ እናም ደረት የመድቃቱ ነገር አስፈላጊ አልመሰለኝም፡፡ ቀስ እያልኹ የቤቱን መብራት እና ድምፅ ተላመድኹት፡፡ አቀማመጤን አስተካክዬም ሰረቅ እያደረግሁ ቀረብ ካሉት “የገላ ነጋዴዎች” ቅኝቴን ጀመርኹ። የቤቱ አጠቃላይ ስፋት በግምት ሁለት ሺሕ ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ እጅግ ሰፊ ወጥ አዳራሽ ነው፤ ግን ደግሞ በተለያየ መንገድ ተከፋፍሏል፡፡ አራት መዓዝን ቅርጽ ያላቸው ሰፋፊ የመጠጥ መሸጫ ባንኮኒዎች፣ በርካታ የመደነሻ መድረኮች አሉት፡፡

ነጭ እና ጥቁር ቀለም ያላቸው ሴቶች ተራ በተራ ወደ መድረኩ እየመጡ የዕርቃን ትርኢት ያሳያሉ፤ ጨርሰው ሲወርዱም ግብዣ ያቀረበላቸውን ሰው ይዘው በአንደኛው የቤቱ ኮርነር በርከት ብለው ወደተደረደሩትና የመኝታ ያህል ተለጥጠው የሶፋ መቀመጫዎች ይዘው እየሄዱ ሥራቸውን በግል ይቀጥላሉ። ልዩ ክፍያ የሚከፍል ደግሞ ሴቶቹን ወደውስጠኛው ክፍል ይዞ እንዲገባ ይፈቀድለታል፡፡ “እዚህ ቤት ግን በርግጥ ኢትዮጵያውያን ይመጣሉ?” - ቀደም ሲል የሰማሁትን መረጃ ተጠራጥሬ እንደገና ለማረጋገጥ ለባለታክሲው ያቀረብኹለት ጥያቄ ነው፡፡ በርግጥ ጥያቄው የሞኝ ይመስላል፡፡ በአዲስ አበባዎቹ የምሽት ዳንስ ቤቶች ውስጥ ተገኝተው በአዳጊ እንስቶች የውስጥ ሱሪ ገንዘብ እየጨመሩ የሚዝናኑ ኢትዮጵያውያንን በኢትዮጵያ ምድር አይቼ እንዲህ በዘመነች አገር የኢትዮጵያ ልጆች ታዳሚ መሆናቸውን መጠየቅ በርግጥ “ሞኝነት” ነው፡፡ ግን ደግሞ የቤቱን አስነዋሪነት ስመለከት በዚህ ቦታ የሀገሬ ልጆች ተሳታፊም ታዳሚም ናቸው መባሉን አምኖ መቀበል ከባድ ኾነብኝ፡፡ መብሰክሰኬ ብዙም ሳይቆይ ከጓደኞቼ የአሻግረሽ ተመልከቺ የቀስታ ጥቆማ ደረሰኝ። በቀላሉ አልታይ አለኝ፡፡ ከተቀመጥኹበት ረጅሙ የባንኮኒ ወንበር ተንጠራርቼ ዐይኔን አሻገርኹ፡፡ ከፍ ካሉት የመደነሻ መድረኮች ዝቅ ብለው ከተደረደሩት መቀመጫዎች ላይ አንዲት ሴት እና ሁለት ወንዶች ተቀምጠው እንቅስቃሴውን ፈዘው ያስተውላሉ፡፡ በመጠጥ ጭምር እየተዝናኑም ይንቀሳቀሳሉ፡፡ ያየኋቸው ከርቀት ቢሆንም ኢትዮጵያውያን መሆናቸውን መለየት አላስቸገረኝም፡፡ ባያውቁኝ ባላውቃቸውም እዚያ ቦታ ቁጭ ብዬ በሌላ የሀገሬ ሰው በመታየቴ ብቻ ሃፍረት ተሰምቶኝ ለመደበቅ ሞከርኹ፡፡ እነርሱ እኔ የተሰማኝ ስሜት የተሰማቸው አልመሰለኝም፡፡ ማንም በዚያ ቦታ ቢኖር ግድ ያላቸው አይመስሉም፡፡ እንደ ውጭ አገር ዜጐቹ ሁሉ እነርሱም ተራ በተራ እየተነሡ ዶላር ይሸልማሉ፡፡

በቃል ያልተመለሰው ጥያቄዬ በተግባር ተመለሰልኝ፡፡ ኢትዮጵያውያኑ በዚያ ቤት ነበሩ፡፡ ባለታክሲው ወዳጄም፤ “የኛ አገር ልጆች በብዛት የዚህ ቤት ደንበኛ አይደሉም። አልፎ አልፎ የእኔ ቢጤ ባለታክሲ ደንበኛ ይዞ ይመጣል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ እንዲህ እንዳንቺ እንግዳ እና አዲስ ሰው ከሀገር ቤት ሲመጣ አሳዩኝ ይልና ለማየት ይመጣል፡፡ ግን ከአንድ ቀን በላይ እዚህ ቤት የሚመጣ ኢትዮጵያዊ በጣም ጥቂት ነው፡፡ አንዳንዱ እዚህ በመምጣቱ ብቻ ራሱን እንደረከሰ ሰው ቆጥሮ ቤተ ክርስቲያን ሄዶ ጠበል ይጠመቃል አትላንታ ካለው ኢትዮጵያዊ በጣም ጥቂት ቁጥር የሚይዙ ሰዎች ግን የቤቱ ደንበኞች ናቸው፡፡እንዲህ ያለ ቤት ስለመኖሩ የማያውቁ ደግሞ በርካቶች ናቸው፤” አለኝ። የቤቱን ታዳሚዎች ኹኔታ በግምታዊ አኅዝ ለማስቀመጥ 300 በሚሆኑ እንግዶች መካከል ከ70 በላይ የሚሆኑ እርቃን ሴቶች ይርመሰመሳሉ፡፡ ከእኔ ጥያቄ እና ከባለታክሲው ወዳጄ መልስ ውጪ በመካከላችን ጸጥታ ሰፍኗል፡፡ ሁለቱ አገጫቸውን እጃቸው ላይ አስደግፈው ጸጥ ብለዋል፤ ተፋፍረዋልም፡፡ እውነት ነው፤ እንዲህ ያለውን ነገር አንድ ላይ ኾኖ መመልከት በራሱ ያስተፋፍራል፡፡ በቤቱ እንደምትሠራ የተነገረኝ አበሻዊ መልክ ያላት ደናሽ አለመምጣት ካሰለቸኝ ከአንድ ሰዓት በኋላ “መጣችልሽ፣ መጣችልሽ!” አለኝ ባለታክሲው ወዳጄ፡፡ ክንፍ ያለኝ ይመስል አኮበኮብኹ፤ ልጅቱን ፍለጋ አንገቴን አንቀዠቀዠኹት፡፡ መካከል ላይ ወዳለው መድረክ የምታመራ፣ ያማረ ተክለሰውነት ወዳላት ወጣት አሳየኝ፡፡ ወደ መድረኩ እየሄደች ስለሆነ ፊቷን ማየት አልቻልኹም፡፡ የሚታየኝ ጀርባዋ ነበር፡፡ አዲስ አበባ እንዳየኋቸው ሴቶች ከእራፊ በላይ በሆነ ጨርቅ ሰውነቷን ሸፍናለች፡፡ ጡቶቿን ሙሉ ለሙሉ የሚሸፍን ጡት ማስያዣ እና ሣሣ ያለም ቢሆን ታፋዋ ድረስ የሚሸፍን ቁምጣ መሰል ነገር ለብሳለች፡፡ ትልቅ ተረከዝ ያለው ቡትስ ጫማም ተጫምታለች፡፡ መድረኩን አስቀድማ ስትደንስበት ከነበረችው ባለነጭ ገላ ሴት ተረክባ የተከፈተላትን የሙዚቃ ምት ተከትላ፣ ቀስ እያለች ወደ መድረኩ ወጣች። ዙሪያውን ከበው የተቀመጡት ታዳሚዎች የቀደመችውን በጭብጨባ ሸኝተው እሷንም በጭብጨባ ተቀበሉ፡፡ የእኔ ዐይን እንዳፈጠጠ ነው፡፡ ጭንቅላቷ በአርተፊሻል፣ ፀጉር ቢሸፈንም መልኳ ሐበሻዊ መሆኑን ለመለየት ነጋሪ አላስፈለገኝም፡፡ በዝግታ የጀመረችውን ዳንስ እያፈጠነችው መጣች፡፡ ሰውነቷ በከፊል የተሸፈነ መሆኑን ስመለከት፣ ምናልባት አንዳች ማኅበረሰባዊ ሞራል በጥቂቱም ቢሆን ተጭኗት ሊሆን ይችላል ስል ጠረጠርኩኹ፤ ግን ደግሞ በቤቱ ውስጥ ከደናሾቹ እንደ አንዷ ኾና መድረክ ላይ ከወጣች በኋላ፣ ሰውነትን በእራፊ ጨርቅ መሸፈኑ ትርጉም አልባ ሆነብኝ፡፡ መጀመሪያውኑ ተወልቆ የተጣለ ነገር ነውና። ልጅቱ እንቅስቃሴዋን ቀጥላለች፡፡

ከመድረኩ ጀምረው ወደላይ የቤቱን አናት እንደምሰሶ ደግፈው የያዙትንና ለዚሁ አገልግሎት ተብለው የተዘጋጁትን ቀጫጭን ብረቶች እየተጠቀመች ስሜትን ለወሲብ በሚቀሰቅስ እንቅስቃሴ ለደቂቃዎች ስትናጥ ቆየች፡፡ ቀጠለችና አንዱን ብረት በአንድ እጇ እንደያዘች የአንድ እግር ጫማዋን አወለቀች፤ አስከትላም ሁለተኛውን ደገመች። በመድረኩ የጽዳት እና የዶላር ሽልማት ሰብሳቢ ሠራተኛ አማካኝነት የወለቀው ጫማ ተነሣ፡፡ ዳንሱ በባዶ እግር ቀጠለ፡፡ ቆየት ብላ የጡት ማስያዣዋን ፈታ ጥላ ከወገቧ በላይ እርቃኗን ሆነች፡፡ “ኦ! አምላኬ! የፈጣሪን ስም ጠራሁ። ሸላሚዎች ተነሡ፡፡ መጠኑ ስንት እንደሆነ መለየት ባልችልም ዶላር ይዘንብላት ገባ፡፡ ቆየት ብዬ እንደተረዳሁት ከቤቱ ደንበኞች ውስጥ ከዐሥር እስከ 100 ዶላር የሚሰጡ ባይጠፉም አብዛኛው ደንበኛ ግን ዘርዝሮ ይዞ አጠገባቸው ይቆምና በተለያየ ስልት እየስደነሰ ዶላሩ አምስት እና ዐሥር ላይ ሲደርስ ቦታው ሄዶ ይቀመጣል፡፡ በቤቱ ውስጥ ራቁት ደናሾቹ በመድረኩ ላይ እያሉ እያዩ ከማስደነስ ውጪ ቀርቦ መንካት የተከለከለ ነው፡፡ ልጅቷ ዳንሷንም እራፊ ጨርቋንም ከሰውነቷ ላይ እያነሣች መጣል ቀጥላለች፡፡ ሥሡን ቁምጣዋን አውልቃ ጥላ በውስጥ ሱሪ ብቻ ቀርታለች፡፡እየተዟዟረች ሽልማቷን ትሰበስባለች፡፡ አዲስ አበባ ላይ ደናሾቹን ባገኘሁ ጊዜ ዳንሱን ሥራ ብለው የያዙት አማራጭ ከማጣት ተነሥተው እንደሆነ አንጀት በሚበላ የችግር ታሪካቸው አዋዝተው ተርከውልኝ ነበር፡፡

በተለይ አንዲት 18 ዓመት በቅጡ የማይሞላት አዳጊ፤ “በትምህርቴ ብዙም ሳልገፋ እናት እና አባቴ ሁለት ታናናሾች ጥለውብኝ ሞተው እነሱን አስተምራለሁ፡፡ የምንኖረው በቀበሌ ቤት ውስጥ ነው፡፡ ረኀብ እና ጥማት ተራ በተራ እየተፈራረቀ ችግር የቤታችን አባል ቢሆንብኝ አንዷን ጐረቤት ተከትዬ ገላዬን ለመሸጥ ጐዳና ወጣሁ፤ ጓደኛዬ እዚህ የመቀጠር ዕድል ሲቀናት ለእኔ ደግሞ መንገዱን አሳየችኝ፤ ከመራብ ገላን መሸጥ፣ ገላን ከመሸጥ ደግሞ አሳይቶ ገንዘብ ማግኘት አይሻልም?” ስትልም ጠይቃኝ ነበር፡፡ ያን ጊዜ “መራብ ይሻላል” እንዳልላት እሷ ሥራውን የመረጠችው መራብ ባስከተለባት መዘዝ እንደሆነ ነግራኛለች። መራብ የሚያመጣውን መዘዝ ደግሞ ምን እንደሚያስታውሰን አላውቀውምና ዝም አልኋት፡፡ የጀመርሽው መንገድ የተሻለ ነው እንዳልል ደግሞ ድርጊቱ አስነውሮኛል። እናም ያኔ ከንፈሬን በሐዘኔታ መጥጬ በደንብ ዝም አልኳት፡፡ ይቺኛዋን ግን ምን ልበላት፡፡ እኔ እሷን እያየሁ ሐሳቤን ሳነሣ ስጥል፣ እርሷ ልብሷን ጥላ ጨርሳ በመጨረሻም እርቃን ገላዋን፣ መለመላዋን ቀርታለች፡፡ አሁን እኔም ኢትዮጵያዊ እንዳትሆን አጥብቄ ተመኘሁ። ይኼኔ እኮ እንዲህ ሆና የምታገኘውን ዶላር ከምትልክላቸው ቤተሰቦቿ ውስጥ አንዱ ወንድሟ እየፈነጨበት ይሆናል ስል አሰብኹ፡፡ የተቀመጡትም የቆሙትም ወንዶቹ በራቁት ገላዋ አፋቸውን ከፍተዋል፡፡ በዛ ሰዓት የሚደንሰው ራቁት ሰውነት የእርሷ ብቻ አልነበረም፡፡ በርካቶች ሥራ ያሉትን እርቃን ዳንስ ተያይዘውታል፡፡

ምን ያህል ሰዓት መድረክ ላይ እንደቆየች ለማስተዋል ባልችልም ሲበቃት ወረደች፡፡ መጨረሻዋን ለማየት በዓይኔ ተከተልኳት፡፡ እንደ ባልደረቦቿ እሷም የመድረኩን ካበቃች በኋላ የግሏን ጀመረች። ተጠርታ መሰለኝ ከወንዶች ጋር ተቀምጣ ስታያት ወደ ነበረች ወጣት ፈረንጅ ሴት ሄዳ ትደንስላት ጀመረች። የዳንሱ እንቅስቃሴ መተሻሸትንም ይጨምር ነበር፡፡ ሲላት ደግሞ ትቀመጥበታለች። ልጅቷን ከዛ በላይ ተከታትሎ መመልከት ለእኔ ሕመም ሆነብኝ፡፡ እንደምንም ብዬ ላነጋግራት ሞከርኩ፡፡ በጉዳዩ ላይ ከወዳጆቼ ጋር ተወያየሁ፡፡ ለማነጋገር ያለው አንድ አማራጭ ለዳንስ መጋበዝ ብቻ ሆኖ ተገኘ። ማነው የሚጋብዘው? ደፋር ከመካከላችን ጠፋ፡፡ እንደምንም ለትንሽ ደቂቃ ብዬ ባለታክሲውን አግባባሁት፡፡ በአንዷ አስተናጋጅ አማካይነት ጥሪ ተላለፈላት፡፡ ቆየት ብላ በውስጥ ሱሪ እና በጡት ማስያዣ መጣች፡፡ ቁርጥ ሐበሻ። እንደመጣች ባለታክሲውን እየተሻሸች መደነስ ጀመረች፡፡ ከየት እንደመጣች ለማወቅ በአማርኛ ሰላምታ ሰጠኋት። በማውቃቸው ጥቂት ትግርኛ ቋንቋ ሞከርኋት፡፡ አሁንም ዝም አለች፡፡ ባለታክሲው እየቀፈፈው መጣ፤ ሊታገሠኝ አልቻለም፡፡ ለመገፍተር የዳዳው ይመስላል። ሰላምታውን በፈረንጅ ቋንቋ አደረግሁና “የሀገሬ ልጅ መስለሽኝ ነው” አልኋት፡፡ ዳንሷን ሳታቋርጥ “የት ነው ሀገርሽ?” አለች። “ኢትዮጵያ”፣ አንገቷን በማወዛወዝ ምላሽ ሰጠችኝ፡፡ እኔ ከዛ አይደለሁም ማለቷ ነበር፡፡ “ከአሥመራ?” አሁንም አንገቷን አወዛወዘች፡፡ “መልክሽ ግን የኛን አገር ሰው ይመስላል” አልኋት፤ ዝም ብላ መወዛወዟን ቀጠለች፡፡ “ይውለቅልህ” ለባለታክሲው ጥያቄ አቀረበችለት፡፡ ያችኑ እራፊ ጨርቋን ልታወልቅ መሆኑ ነው፡፡ “አልፈልግም፤ አልፈልግም” አለና ተቻኩሎ ከኪሱ ካወጣቸው ዶላሮች መካከል አምስት ዶላር ሰጣት አሜሪካን ሀገር ባለታክሲን ከሌላው ሰው ለየት የሚያርገው በርካታ ዝርዝር ዶላሮች በኪሱ መያዙ ነው፡፡

እንደ ሌላው ሰው በየማሽኑ ላይ ካርድ ሲጭር አይውልም። “ዐሥር ዶላር ነው” ስትል አምስት ዶላር ጭማሪ ጠየቀችው፤ እንዲያቆያት በዐይኔ ብለማመነውም ፈቃደኛ አልሆነም። ዐሥር ዶላር ጨመረላትና እንድትሄድለት “አመሰግናለሁ” አላት፡፡ ምስጋናውን በፈረንጅ ቋንቋ ነበር ያቀረበላት፡፡ እሷም ዶላሩን ተቀብላው “አመሰግናለሁ” አለችው። መልሱ ግን በአማርኛ እንጂ በፈረንጅኛ አልነበረም።ሁለታችንም በድንጋጤ “እንዴ?” የሚል ቃል አወጣን፡፡ እኔማ ከተቀመጥኹበት ተነሥቼ ይዤ ላስቀራት ምንም አልቀረኝም። ፈገግ ብላ “ያቐንየለይ” ስትል ምስጋናውን በትግርኛ ጨምራልን፣ አረማመዷን አፍጥና ግራ አጋብታን ወደመጣችበት ተመለሰች፡፡ ዳንስ ቤቱን ለማየት ከመሄዴ በፊት ስለሐበሻዊ መልኳ ደናሽ የነገሩኝ ኢትዮጵያውያን ልጅቷ ኤርትራዊ ስለመሆኗ ሳይጠራጠሩ ነበር ያወሩኝ፡፡ ኤርትራውያን ባገኘሁ ጊዜም ስለዚችው ልጅ ጠይቄያቸው ኢትዮጵያዊ ስለመሆኗ ነው ያወሩኝ፡፡ አብረውኝ የመጡት ልጆችም ልጅቱ ኤርትራዊ ስለመሆኗ ቅንጣት ታክል ጥርጣሬ አልነበራቸውም፡፡ሁለቱም ከኛ ወገን አይደለችም ሲሉ፤ እዚያ እና እዚያ አሽቀንጥረው ሊጥሏት ይሞክራሉ፡፡ ዋናው ምክንያታቸው ደግሞ በድርጊቱ ማፈራቸው ነው፡፡ የልጅቷ ዜግነት የማወዛገቡ ሌላው ምክንያት ራሷ ልጅቷ መሆኗ ገባኝ። በሁለቱም ቋንቋ ትናገራለች፤ መልኳም የሐበሻ ነው፡፡ ለእኔ ግን መምጫዋ አላስጨነቀኝም፡፡ እሷ ከየትኛውም ትምጣ፤ ከሁለቱም ሀገር ቀያቸውን ጥለው የሚሰደዱ ዜጎች፤ ወይ በትምህርት፣ በፖለቲካ ጉዳይ አሊያም ሥራ ፍለጋ ነው፡፡ “እንጀራ ፍለጋ 15 ሺሕ ኪሎሜትር ተጉዞ ገላን በአደባባይ አራቁቶ ለሰፊ ሕዝብ መሸጥን ምን አመጣው?” አላናገረችኝም እንጂ ይህችንም እንደ አዲሳባዎቹ ልጠይቃት ያሰብኹት ጥያቄ ነበር፡፡

ምናልባትም “ከምራብ ብዬ” ነው ትለኝ ይሆናል፡፡ የሷ ግን እንደአዲሳባዎቹ መልስ አልባ አያደርግም፤ “ስንት እንጀራ ለመብላት ነው?” እላት ነበር፡፡ ለእኔ ሰቅጣጭ ከሆነብኝ ከዚህ ቤት ወጥተን ያመራነው ወደ ኢትዮጵያውያን ጭፈራ ቤት ነበር። መቼም “ከሺሻ እና ከዳንስ ቤት አትወጪም ወይ?” እንዳትሉኝ እኔ ያየሁት እንዳይቀርባችሁ ከሚል እሳቤ ነው!! ሌላ ሌላውንም ያየኹትን፣ የታዘብኹትን ያህል ቀስ እያልኹ አወጋችኋለሁ፡፡እናም በዚህ ጭፈራ ቤት በመጠጥ ተሟሙቀው፣ሲያሻቸው እየተሻሹ ሲላቸው እየተሳሳሙ፣ሲላቸው እየቆሙ፣ሲፈልጉ ደግሞ ተቀምጠው ሺሻቸውን እያጨሱ፤በጭሱ ደግሞ ታፍነው ልባቸው እስኪጠፋ በሀገራቸው ዘፈን እየጨፈሩ ያየኋቸው ጥንዶች እጅግ ጨዋ ሆነው ታዩኝ። የአስነዋሪ እና የአኩሪ ተግባር መለኪያው ጠፋብኝ፡፡ በአሜሪካ ቆይታዬ በአገሬ የማውቀውን የአስነዋሪ እና የአኩሪ ታሪክ መለኪያ ካጠፋብኝ ሌላው የጥቂት ኢትዮጵያውያን ተግባር አንዱ ደግሞ የግብረሰዶማውያን ነገር ነው፡፡ለአሜሪካኖቹ ሳይቀር አስጨናቂ በሆነው ግብረሰዶማዊነት ተዘፍቀው ያየኋቸውና ታሪካቸውን የሰማሁት ኢትዮጵያውያን እስካሁን አስጨንቀውኛል። ጎዳና የወጡ ኢትዮጵያውያንን ማየት እነዚህኞቹን እንደማየት አልከበደኝም፡፡ ግብረሰዶማዊነት በአሜሪካ መባባሱ እና ቀስ በቀስ በተለያዩ ግዛቶች ለጋብቻም እየተፈቀደ መሄዱ የኢትዮጵያንም ራስ ምታት ሆኗል። አንዲት እናት ለአቅመ አዳም የደረሰ ወንድ ልጇ “ማሚ ጓደኛዬን ላስተዋውቅሽ” ሲል በሰጣት ቀጠሮ ስላጋጠማት ነገር ያወጋችኝን ደግሞ እስቲ ልንገራችሁ። (ይቀጥላል)

አንዳንዴ ምን እንደማስብ ታውቃላችሁ? የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ፍፁም ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ አዲስ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግኝት የሚፈጥርልን ብናገኝ (ቻይናን ምን ይሳናታል?) በገንዘብ ባንችል እንኳን በ”ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ” ስም እንማጠናቸው ነበር… (ቻይና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ስታውቅ አይደል?)

ወዳጆቼ፤ የጥምቀት በዓል እንዴት አለፈ እባካችሁ? በሸጋ ያለፈ ይመስለኛል (እኔ ከናንተ ባላውቅም) ከሁሉም ያስደመመኝ ግን ምን መሰላችሁ? በጥምቀት ይወረወር የነበረው ሎሚ ተረት ሆኖ (እንደ ድህነት? ማለት ነው) ዘንድሮ በፕሪም ተተክቷል የሚባል ነገር ሰምቻለሁ፡፡ “ወጭ ለምኔ” ያሉ የዘመኑ ወጣቶች ደግሞ (በሬ ለምኔ እንደሚባለው) የሞባይል ነምበራቸውን ቆነጃጅቱ ደረት ላይ ሲወረውሩ እንደዋሉም የአውዳመት የወሬ ምንጮቼ ሹክ ብለውኛል፡፡ በደቡብ አፍሪካው የባለፈው ሰኞ የብሄራዊ ቡድናችን ግጥምያ እለት የተባለውን ሰምታችሁልኛል? “ውበት ሲለካ የኢትዮጵያ ሴቶች ናቸው ለካ!” የሚለውን ማለቴ ነው፡፡ (ለነገሩ ሲያንሳቸው እኮ ነው!!) ነገርዬውን ዝም ብዬ ሳስበው ግን የኢትዮጵያን እንስቶች ውበት ድንገት ያጐሉት ያለፈው የአፍሪካ ዋንጫ ሻምፒዮን ከሆነችው ዛምቢያ ጋር ገጥመው (ያውም በጐደሎ ተጫዋቾች) ድንቅ የኳስ ጥበብ ያሳዩት የብሄራዊ ቡድናችን አባላት ይመስሉኛል - (ያዳኑን እነ አዳነን ማለቴ ነው!) የሴቶቻችን ውበትማ አዲስ ክስተት አይደለማ!! እኔ የምለው ግን… በኢቴቪ ቀርቦ አስተያየቱን የሰጠ አንድ

በኢትዮጵያ እግር ኳስ ያበደ አድናቂ፤ ቡድናችንን ከእነሜሲ ጋር ሁሉ ሲያነፃፅር እንደ ነበር ሰምታችኋል? (ቢጋነንም ከጋለ ስሜት የመነጨ ነው ብለን እንለፈው) በነገራችሁ ላይ… ይሄ ህዳሴያችን ብዙ ታሪኮቻችንን እያደሰልን አይመስላችሁም! (በእድል እኮ አይደለም በትጋት እንጂ!) ከህዳሴው ጋር ያልታደሰልን ዋናው የህይወታችን ክፍል ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ? ያልታደለው ፖለቲካችን ብቻ!! እንኳንስ ሊታደስ ቀርቶ ጭርሱኑ ወደ ኋላ… ወደ ጥንቱ የጨለማ ዘመን (dark age) እየጐተተን፣ የዓለም መሳቂያ መሳለቂያ ሊያደርገን ዳር ዳር እያለ እኮ ነው! ፖለቲከኞችን በማሰር፣ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ጋዜጠኞች ለስደት በመዳረግና ወህኒ ቤት በመከርቸም፣ የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ነፃ እንቅስቃሴ በማፈን፣ በሙስናና በመልካም አስተዳደር እጦት፣ በሰብአዊ መብት ጥሰት፣ ወዘተ… ኢትዮጵያ በተደጋጋሚ ስሟ እየተነሳ መሆኑ ፀሃይ የሞቀው አደባባይ ያወቀው እውነት ነው፡፡ በእርግጥ እንዲህ ያለውን ውንጀላ ባልወለደ አንጀታቸው የሚሰነዝሩት የኢትዮጵያ በጐ ነገር የማይዋጥላቸው እንደ ሂዩማንስ ራይት ዎች ያሉ ጨለምተኛ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እንደሆኑ ሁሌም ገዢው ፓርቲያችን ይነግረናል (እንዳንሳሳት ብሎ እኮ ነው!) ችግሩ ግን ምን መሰላችሁ? እዚሁ ከምርጫ ቦርድ ህጋዊ ሰርተፊኬት ተሰጥቷቸው የሚንቀሳቀሱትም ህጋዊ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተሟጋቹን ውንጀላ አንድም ሳያስቀሩ ይቀበሉታል፡፡

(ታዲያ ምን ተሻለ?) ምን መቀበል ብቻ… “መች ተነካና… ይታያል ገና!” ባይ ናቸው፡፡ (የገዢውን ፓርቲ ጉድ ማለታቸው እኮ ነው!) እኔ የምለው ግን… የአገር ሽማግሌዎች ቡድን መሪ የሆኑት ባለውለታችን ፕሮፌሰር ኤፍሬም ይስሃቅ ፓርቲዎችን የማስታረቅ በጐ ሚናቸውን እንዴት ዘነጉት? ለነገሩ በእሳቸውም አይፈረድም እኮ! (የአውሮፕላን ወጪ ገደላቸዋ!) እንዴ… በ97 የፖለቲካ ቀውስ ጊዜ ታስረው የነበሩትን የቅንጅት አመራሮች ከመንግስት ጋር ለማስማማት ከአሜሪካ ኢትዮጵያ የነበረውን ጉዞ የውሃ መንገድ አድርገውት ነበር እኮ! ያውም በገዛ ገንዘባቸው እየተመላለሱ፡፡ ግን ምናለ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የሚመላለሱበትን የአየር ትኬት ስፖንሰር ቢያደርጋቸው? (የአገር ጉዳይ አይደለም እንዴ?!) ለማንኛውም ግን ፕሮፌሰሩ አንዴ እንደምንም ወደ አገራቸው ጐራ ብለው ኢህአዴግንና ተቃዋሚዎቹን “አንተም ተው! አንተም ተው!” ቢሏቸው ሳይሻል አይቀርም ባይ ነኝ፡፡

(እረስቼው! ምርጫ ቦርድም ለካ ሌላው የፓርቲዎች የኩርፊያ ሰበብ ነው) እሱ እንኳን እርቅ ሳይሆን “ማጥራት” ነው የሚሻለው፡፡ አንዳንዴ ምን እንደማስብ ታውቃላችሁ? የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ከፖለቲካ ወገንተኝነት ፍፁም ነፃ መሆኑን የሚያረጋግጥ አዲስ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ግኝት የሚፈጥርልን ብናገኝ (ቻይናን ምን ይሳናታል?) በገንዘብ ባንችል እንኳን በ”ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ” ስም እንማጠናቸው ነበር… (ቻይና ነፃና ፍትሃዊ ምርጫ ስታውቅ አይደል?) እንዴ… ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ከ15 አመት በኋላ በጐ እንቅስቃሴ የጀመረው እግር ኳሳችን እንኳ የእነቬንገርን ቀልብ ስቧል እየተባለ እኮ ነው፡፡ ፖለቲካችን ግን ይኸው 21 አመት ወደኋላ መምዘግዘግ ይዞላችኋል - ያውም ህዳሴያችንን ይዞ (ወይ ነዶ አሉ!) አያችሁ… ይሄ ክፉ ፖለቲካችን የጀመርኩትን የጥምቀት ወግ ሳልጨርስ እንዴት ጐትቶ ውስጡ እንደዶለኝ! (ፖለቲካችን እርግማንና ወቀሳ ምሱ ነው አሉ!) እኔ የምለው… በዘንድሮ የጥምቀት በዓል መዲናዋ እንዴት እንደፀዳችና እንደተዋበች በደንብ አስተውላችኋል? እንዴ… ከተማዋ 125ኛ ዓመት ልደቷን አንድ አመት ሙሉ ስታከብርም እኮ እንዲህ አላማረባትም! (አክብሮ መና ይሏል ይሄ ነው!) እውነቴን ነው የምላችሁ… የመዲናዋ ወጣት በዓሉን ያከበረው “ለጥምቀት ያልሆነ ከተማ…” በሚል አዲስ ምሳሌያዊ አባባል ይመስላል፡፡

(ለጥምቀት ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ እንዲሉ!) ቆይ ግን ያልፀዳና ያልተዋበ የመዲናዋ ስፍራ አለ እንዴ? (ማዘጋጃ ቤት ሲያሾፍ እንደኖረ የገባን አሁን ነው!) ለወትሮው የሽንትና የቆሻሻ ክምር የነበሩ ስፍራዎች ሁሉ ፀድተውና በተለያዩ ቀለማት ተኳኩለው “ሸገር” ተውሰን ያመጣናት ከተማ ልትመስለን ምን ቀራት? መርካቶ ሰባተኛ አካባቢ እንዴት በባንዲራና በፊኛ አሸበርቆ እንደነበር መስተዳድሩ አይቶት ይሆን? (ማን ነበር “ይደገም ቅዳሜ” ያለው…) ከምሬ ነው… መቼም አይቶት ከሆነ የመዲናዋ ልደት “በህዝብ ጥያቄ በድጋሚ ይከበራል” ማለቱ አይቀርም! እኔ ግን የልደቱን በድጋሚ መከበር ምንም ቢሆን እንደማልደግፍ ከወዲሁ አቋሜን ልገልፅ እወዳለሁ፡፡ እንደ 34ቱ ፓርቲዎችም ፒቲሽን ማሰባሰብ ከጀመርኩ አንድ ሁለት ቀናት አልፎኛል፡፡ አያችሁ… ባለፈው ተመክሮ እንደተገነዘብነው መስተዳድሩ የፓርቲና የፌሽታ ነገር አይሆንለትም፡፡ (ፍንዳታ ቢጤ ነው!) የመዲናዋን 125ኛ አመት ከአንድ አመት በላይ እኮ ነው ያከበረው፡፡ (ለመሆኑ ጊነስ ላይ ተመዘገበለት ይሆን?) እናላችሁ… ራሴ ያነሳሁትን የይደገም ጥያቄ ራሴ መቃወሜን እወቁልኝ፡፡ አንድ ጥያቄ ግን አለኝ፡፡ መስተዳድሩ የመዲናዋን ልደት ከአንድ አመት በላይ ሲያከብር (ራሱ ነው ያለን!) ምን ማስታወሻ የሚሆን ነገር ለከተማዋ ሰራላት? (ከፕሮፓጋንዳው ውጭ ማለቴ ነው!) ይኸውላችሁ… እኔ ከጥምቀቱ የወጣቶች ቡድን ምን ቁምነገር ቀሰምኩ መሰላችሁ? የመዲናዋ ወጣት ሲፈልግና ልቡ ያመነበት ጉዳይ ሲሆን እንደንብ መንጋ ነው - የያዘውን ስራ ዶግ አመድ ያደርገዋል፡፡ አድምቶ ይሰራዋል! (በኢህአዴግ ቋንቋ!) ይታያችሁ… የፅዳት ሠራዊት የለ! የህዝብ ንቅናቄ የለ! 1ለ5 አደረጃጀትማ ጭርሱኑ ትዝ ያለውም የለ!! አያችሁልኝ… ወጣት ባመነበት ጉዳይ ላይ እንዲህ አጀብ ያሰኛል - ያውም ያለ አንዳች የካድሬ ፕሮፓጋንዳና አጀብ!!

እኔማ ምን አሰብኩ መሰላችሁ? ጥምቀት ለምን ሁለቴ አይከበርም አልኩኝ (ግን ለራሴ ነው) (ከተማዋ እኮ አበባ መሰለች!) ጥምቀት እንዲህ ከሆነ ግን ለምንስ የፖለቲካ ጥምቀት፤ የዲሞክራሲ ጥምቀት፣ የልማት ጥምቀት፣ የመልካም አስተዳደር ጥምቀት፣ የጥበብ ጥምቀት፣ የፕሬስ ነፃነት ጥምቀት፣ የመድብለ ፓርቲ ስርአት ጥምቀት፣ ፍትሃዊ የሃብት ክፍፍል ጥምቀት ወዘተ… ወዘተ… አያሌ የህዳሴ ጥምቀቶችን አይኖሩንም ስልም ተመኘሁ - ሁሉም በአንድ መንፈስ ከልቡ የሚያከብረው፡፡ ባይገርማችሁ… በፕሮፓጋንዳ ያልተካበደ ህዳሴ እንዴት እንዳማረኝ አልነግራችሁም (አምሮት መብቴ መሰለኝ!) ውድ አንባቢያን፡- ፕሮፓጋንዳ ያልበዛበት ፖለቲካ የት እንደሚገኝ የምታውቁ ከሆነ ብትጠቁሙኝ ወሮታውን እከፍላለሁ፡፡ እኔ የምለው ግን… እኔ ብቻ ነኝ ወይስ እናንተም ናችሁ የፖለቲካ ህዳሴ የናፈቃችሁ? ለነገሩ ባይናፍቃችሁም አይፈረድባችሁም! (ተስፋ ቆርጣችሁ እኮ ነው!) እንዴ ፖለቲካችን “ከርሞ ጥጃ”፣ “ታጥቦ ጭቃ” ሲሆንባችሁስ? እውነቱን ልንገራችሁ አይደል… በጥንቱ አካሄድማ የፖለቲካ ህዳሴን መመኘት ባዶ ህልም ከመሆን ፈፅሞ አያልፍም፡፡ ለውጥ የምንሻ ከሆነ በብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድናችን ላይ የምናየውና የምንሰማው አይነት አዲስ አቅጣጫና አካሄድ ልንከተል ግድ ይለናል፡፡በእርግጥ በአንድ ጀንበር ስር ነቀል ለውጥ መጠበቅ ሲበዛ የዋህነት ነው፡፡ እንኳንስ በጦቢያ ፖለቲካ ቀርቶ በየትም አገር ቢሆን ሁሉም ነገር ቀስ በቀስ እያደገ ነው የሚመጣው፡፡

የአፍሪካ ተቃዋሚዎች ስልጣንም ሆነ ዲሞክራሲ ዛሬውኑ ካልተንበሸበሽን ብለው የሙጥኝ ሲሉባቸው ፈረንጆቹ ምን እንደሚሉ ታውቃላችሁ? “ዲሞክራሲ ሂደት ነው!” ይሉና ይገላገሏቸዋል፡፡ እንዴ ምን ያድርጉ ታዲያ? ለነገሩ የእኛዎቹንም እኮ እናውቃቸዋለን… ምርጫን የሞት ሽረት ጉዳይ ያደርጉት የለም እንዴ! ለዚህ እኮ ነው የሥነልቦና ትምህርት የሚያስፈልጋቸው፡፡ ከምሬ ነው… ፖለቲከኞቻችን የAttitude ለውጥ ካላመጡ ፖለቲካው መቼም አይለወጥም! እኔማ የስነልቦና ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ አሰልጣኝም (coach ወይም mentor ነገር) ይፈልጋሉ ባይ ነኝ! (ኢህአዴግንም ይጨምራል!) ፖለቲካ እኮ ብስለትም ብልህነትም ይፈልጋል፡፡ አጉል ብልጣብልጥነት ብቻውን የትም አላደረሰማ!! (ካላመናችሁኝ ኢህአዴግን ተመልከቱት!) ከችኩሉ ጥላቻ ተኮር ፖለቲካችን የምንላቀቀውም በጥሩ አሰልጣኝ ድጋፍ ይመስለኛል (የፖለቲካ ሰውነት ቢሻው ቢገኝማ ሽረት ነበር!) የሚገርማችሁ ግን በፖለቲካው ውስጥ ፀጉራቸው እስኪሸብት ኖረውበትም ዘንድሮም ቅንጣት ታህል ያልተለወጡ አያሌ ፖለቲከኞች በጦቢያ ምድር ሞልተው መትረፋቸው ነው፡፡ ልብ አድርጉ! እኔ ፈፅሞ የአገሬን ፖለቲከኞች የማንኳሰስ ድብቅ አጀንዳ የለኝም፡፡ የማንም ተላላኪም አይደለሁም! (ለምሳሌ የሻዕቢያ!) ራሳቸው ፖለቲከኞቻችን እኮ ራሳቸውን ለማንኳሰስ ማንንም አያክላቸውም!! (እዳ እኮ ነው የገባነው!) ባለፈው ሰሞን የኢንጂነር ሃይሉ ሻውል ፓርቲ የቀድሞ አመራሮች የቆየ ውዝግባቸወን እንደ አዲስ ሊጀምሩ መሆኑን ሰምቼ እንዴት እንደተቃጠልኩ አልነግራችሁም፡፡

እስቲ ይታያችሁ… ከኢህአዴግ ጋር የማይቀርላቸው “ልፍያ” ሳያንሳቸው እርስ በእርስ ፍልምያ መግጠማቸው ምን የሚሉት እዳ ነው (ወይስ የወዳጅነት ግጥምያ መሆኑ ነው!) እንዲህ ያሉት እኮ ፖለቲካም፣ ፓርቲም ወደሚለው ጉዳይ ከመግባታቸው በፊት ለራሳቸው ክብር መስጠትን የግድ መማር አለባቸው (እድሜማ አላስተማራቸውም!) ፈረንጆቹ postive attitude, self esteem ምናምን የሚለውን በደንብ በውስጣቸው ካሰረፁ በኋላ በማንኛውም ፈተናና ወከባ ተከበውም ቢሆን ፅናትና ብርታት ካላቸው ስኬት እንደሚቀዳጁም መማር፣ መሰልጠን፣ መለማመድ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የምርጫ ሰሞን ወከባን ለማስቀረት ብልሃቱ ዝግጅት ብቻ ነው! ኢህአዴግ ከችግሩ (ኃጢያቱ) ነፃ ነው እያልኩ ግን እንዳይመስላችሁ፡፡ የችግሩ እናት ማን ሆነና! በነገራችሁ ላይ ለኢህአዴግ የሚሰጠው ስልጠና ማተኮር ያለበት… ጦቢያን ለማሳደግ፣ ለማበልፀግ፣ ከድህነት ለማውጣት፣ ዲሞክራሲን ለማስፈን ወዘተ ከላይ የተቀባሁት እኔና እኔ ብቻ ነኝ የሚለው ክፉኛ የተጣባው አመለካከቱ ላይ ነው፡፡ “ፀሃዩን ንጉስ” በመቃወም ወደ ትግል የገባ ፓርቲ እንዴት ያንኑ የተቃወመውን አመለካከት ያቀነቅናል? (ታሪክ ራሱን ይደግማል አሉ!) ይሄ ሁሉ ስጋት ከምን የመጣ እንደሆነ እንድታውቁልኝ እሻለሁ! አያችሁ… እስከዛሬ ኦክስፎርድ ዲክሽነሪ Famine የሚለውን ቃል Food Shortage, scarcity, starvation ወዘተ በማለት ከፈታ በኋላ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ምሳሌ የሚጠቅሰው ጦቢያን እንደነበር እናውቃለን አይደል! አሁን ደግሞ ሳናስበው “ኋላ ቀር ፖለቲካ” ለሚለውም ቃል ዳግም አገራችን በዲክሽነሪው ላይ እንዳትጠቀስና ዳግም ሼም በሼም እንዳንሆን ክፉኛ ሰግቻለሁ፡፡

እናላችሁ… አገሬን እወዳለሁ የሚል ዜጋ ሁሉ ጦቢያን ከኋላቀር ፖለቲካ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማውጣት ከፍተኛ እርብርቦሽ ያደርግ ዘንድ ጥሪ ቀርቦለታል፡፡ እኔ የምለው ግን… ሰሞኑን በድራማ መልክ በኢቴቪ የሚተላለፈውን ማስታወቂያ አይታችሁልኛል - በሁለት ጫማ የሚገዙ እንስቶች የተሰራውን ማለቴ ነው፡፡ በስተመጨረሻ ላይ አንደኛዋ አዲስ የገዛችው ጫማ ተረከዟን እንደላጣትና እግሯን እንዳቃጠላት ለጓደኛዋ በምሬት ስትነግራት “በደንብ ሳትመርጪ ለምን ገዛሽ?” ትላታለች (ዋጋሽን አገኘሽ በሚል ስሜት!) ለካስ ነገርዬው ለሚያዝያው የአዲስ አበባና አካባቢ ምርጫ የተሰራ ማስታወቂያ ነው፡፡ እኔ እኮ የቻይና ጫማ ገዝታ የተቃጠለች ነበር የመሰለኝ፡፡ (ቀላል ተሸወድኩ!) ለነገሩ የማይሆን ፓርቲ መምረጥ ከቻይና ጫማም የበለጠ ሊያቃጥል ይችላል፡፡ (ፈጣሪ ይጠብቀን እንጂ!) በመጨረሻ በምርጫው ለሚሳተፉ ፓርቲዎች (ከ29ኙ ውጭ) ሁሉ የሚመች ነጠላ ዜማ እንዳገኘሁላቸው ሳበስራቸው ኩራት ይሰማኛል (ቃል በቃል መቅዳት ያኮራል ተብሎ የለ!) እንዲህ የሚል ነው የዜማው ግጥም፡- በቃ በቃ አልፈልግም ሌላ ላይመች ላይደላ… (ከጫማው ማስታወቂያም ጋር ይሄዳል አይደል? በምርጫው የምትሳተፉ ፓርቲዎች ይመቻችሁ!!) ,

  • ቤቶቹ ከቤተ መድኃኔዓለም እና ቤተ ዐማኑኤል አጠገብ የተሠሩ ነበሩ 
  • በልደት ክብረ በዓል የቱሪስቶች ቁጥር መቀነሱ ኅብረተሰቡን አስደንግጧል 

በቅዱስ ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም ከዐሥራ አንዱ ውቅር አብያተ መቅደስ ጋር በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ አራት ጥንታውያን ቤቶች በእሳት ቃጠሎ መውደማቸው ተገለጸ፡፡ ባለፈው እሁድ ለሰኞ አጥቢያ መንሥኤው ባልታወቀ ምክንያት በተነሣው የእሳት ቃጠሎ የወደሙት አራት ቤቶች የሣር ክዳን ያላቸው ፎቅ ቤቶች ሲኾኑ፣ የላሊበላን ጥንታዊ የቤቶች አሠራር የሚያሳዩ በመኾናቸው እየተጠገኑ እንዲጠበቁ በዩኔስኮ የዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ ነበሩ፡፡ በቃጠሎው የወደሙት ጥንታውያኑ ቤቶች፤ ከቤተ ክርስቲያኒቱ የአብነት ትምህርቶች መካከል በቅኔና ዜማ ትምህርት መስጫነት ሲያገለግሉ እንደቆዩ ተገልጧል፡፡ ገኛ ቦታቸውም ከዐሥራ አንዱ አብያተ መቅደስ መካከል በታላቁ ቤተ መድኃኔዓለም እና በቤተ ዐማኑኤል አጠገብ ከ20 - 30 ሜትር ርቀት ላይ መኾኑ፣ የገዳሙ አስተዳደር ጽ/ቤት ለቅርሶቹ ደኅንነት ትኩረት ሰጥቶ በቂ ጥበቃና ክብካቤ እንደማያደርግ በካህናቱ እና ምእመናኑ የሚነሡበትን ስጋቶችና ተቃውሞዎች ያጠናከረ ነው ተብሏል፡፡ ለአዲስ አድማስ አስተያየታቸውን የሰጡ የከተማው ነዋሪዎች እንደሚያስረዱት÷ የቃጠሎ አደጋው በደረሰበት ዕለት ሌሊት በሁለቱም አብያተ መቅደስ አካባቢ የገዳሙ ጥበቃ አባላት አልነበሩም፡፡

ከሙስና እና ብልሹ አሠራር ጋር ተያይዞ ጥያቄ የሚነሣባቸውና ላለፉት ስምንት ዓመታት በአስተዳዳሪነት የቆዩት የገዳሙ መምህርም ቃጠሎው በደረሰበት ስፍራ የተገኙት ከሁለት ቀናት በኋላ ነው፡፡ ቤቶቹ ሰው በማይኖርበትና ‹‹ኮር ዞን›› ተብሎ በዩኔስኮ በሚታወቀው ለቅርሶች የተለየ ስፍራ የሚገኙ ኾነው ሳለ የተከሠተው ይኸው አደጋ፣ ‹‹በአስተዳደሩ ላይ እየተጠናከሩ የመጡትን ተቃውሞዎች ትኩረት ለማስቀየስ የተፈጠረ›› አድርገው እንደሚወስዱት የስፍራው ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል በቅ/ላሊበላ ደብረ ሮሃ ገዳም በአንድ ጊዜ በተደረገው የ160 በመቶ የቱሪስቶች ዋጋ ጭማሪ ሳቢያ ዘንድሮ በተከበረው የልደተ ክርስቶስ (ቤዛ ኵሉ) እና ጥምቀት በዓላት ላይ የተገኙት የውጭ ቱሪስቶች ፍሰት ቀንሶ መስተዋሉን የዜናው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ የቱሪዝሙ ባለድርሻ አካላት በበቂ ባልመከሩበት ኹኔታ በአንድ ወገን ውሳኔ ገቢን ከፍ ለማድረግ ብቻ ታስቦ ከጥር አንድ ቀን ጀምሮ በተፈጸመው በዚሁ ጭማሪ ብር 350 የነበረው የቱሪስት መግቢያ ብር 1000 እንዲኾን ተደርጓል፡፡ ባለፈው ዓመት የጥምቀት በዓል ብቻ ከአንድ ሺሕ በላይ የውጭ ቱሪስቶች መገኘታቸውን ያስታወሱት ምንጮቹ፣ በዚህ ዓመት ግን ለቱሪስቱ አስቀድሞ ከተገለጸለት የመግቢያ ዋጋ በተለየና በራቀ አኳኋን ጭማሪ በመደረጉ ምክንያት ቁጥሩ በግማሽ አንሶ መገኘቱን ገልጸዋል፡ ፡ በተለይም ያለቱር ኦፕሬተርስ በግላቸው ለጉብኝት የመጡ ቱሪስቶች ከስፍራው ከደረሱ በኋላ በናረው የመግቢያ ዋጋ ምክንያት ውቅር አብያተ መቅደሱን ሳይጎበኙ የተመለሱ እንዳሉ፣ ከእኒህም መካከል ላሊበላን መጎብኘት አዳጋች መኾኑን ለሚዲያዎች ሐሳብ የሰጡ እንደሚገኙበት ተነግሯል፡፡

የቱሪስት ፍሰት መቀነሱ በዋናነት የላሊበላ ውቅር አብያተ መቅደስ ያለውን የቱሪስት መስሕብነት ማእከል በማድረግ የተመሠረተውን የአስተዳደሩን የልማት እንቅስቃሴና የኅብረተሰቡን ኑሮ ይጎዳል ያሉት ምንጮቹ፣ በከተማው ነዋሪ ላይ ከፍተኛ ድንጋጤ መፍጠሩንም ለዝግጅት ክፍሉ አስረድተዋል፡፡ በልማትና በቅርስ ሀብቱ ተጠቃሚ ከመኾን አኳያ አካባቢው ‹‹ዕድለ ቢስ ነው›› የሚሉት የከተማው ነዋሪዎች፤ ከተማውን ከሌሎች ከተሞች ጋር ከሚያገናኙ መንገዶች አንሥቶ የተሟላ የሆስፒታል መገልገያ ዕቃዎችና የሕክምና ባለሞያዎች ያላገኘውና አገሪቱን በቱሪዝም ተጠቃሚ ሊያደርግ የሚችለው ላሊበላ:- ለመልካም አስተዳደር መስፈን የሚያሰማው ጩኽት ሰሚ ያጣ የቁራ ጩኸት እንዳይኾን በድጋሚ ጥያቄያቸውን ለማቅረብ መገደዳቸውን አስታውቀዋል፡፡

አንድ የአገራችን ገጣሚ ስለ አይጥ፣ ስለድመት፣ ስለውሻና ስለሰው የፃፈው ግጥም ጭብጡ በስድ ንባብ ቢታሰብ የሚከተለውን ተረት ይመስላል፡፡

አንዲት አይጥ ከዕለታት አንድ ቀን “ድመት” የሚል ግጥም ትጽፋለች አሉ፡፡ የግጥሙ ይዘት “ድመት ባይርባት ኖሮ እኔን አሳዳ አትበላኝም ነበር” የሚል ነው፡፡ አይጥ የፃፈችውን ግጥም ድመት ታገኛለች፡፡ ድመትም “አይጥ” የሚል ግጥም ትጽፋለች - እንደምላሽ መሆኑ ነው፡፡

አይጥና ድመት የፃፉትን ግጥሞች ሰው ያገኛል፡፡

ሰውየው፤ የቤቱ ባለቤት መሆኑ ነው፤ እጅግ አድርጐ ይናደዳል፡፡ ወረቀት ጽፈው በማየቱ እንጂ ስለምን እንደፃፉ አላነበበውም፡፡ ብቻ በንዴት

“አሃ! አይጥና ድመት በእኔ ላይ ግጥም መፃፍ ከጀመሩ፤ ተስማምተው ተነሱብኝ ማለት ነው። አድማ ነው! በጭለማ ወረቀት መበተን የመጥፎ ጊዜ ምልክት ነው፡፡ ትውልዱ ከፋ ማለት ነው። ስለዚህ እርምጃ መውሰድ ይገባኛል!” ሲል አሰበ፡፡ በመጨረሻም እንዲህ የሚል ውሳኔ አሳለፈ፡፡

“በቃ ሁለቱም ይቀጡ

ለዚያችም ወጥመድ ዘርጉ

ለዚችም ገመድ አምጡ!”

በትዕዛዙ መሠረት ወጥመድ ተዘረጋና አይጢት ተያዘች፡፡ ድመትም በገመድ ተጠፍራ ታሠረች። አይጥ ልትሞት ወደማጣጣሩ ደረሰች፡፡ ድመት በታሰረችበት እህል ውሃ አጥታ በረሃብ ልትሞት ተቃረበች፡፡

አይጥ ድመትን፤ “ለባለቤቱ ከምታሳብቂ፣ ልብ ካለሽ መልስ አትጽፊልኝም ነበር?” አለቻት፤ ወጥመድ ውስጥ ሆና!

ድመትም፤ ብስጭትጭት ብላ፤

“ቀጣፊ ነሽ! የፃፍኩልሺን መልስ ለጠላት አሳልፈሽ ከመስጠት አታነቢውም ነበር? በግልጽ አቋሜን ትረጂ ነበር! ከእንግዲህማ ስፈታ ቁም - ስቅልሽን ባላሳይሽ ዕውነት ድመት አደለሁም!” በማለት ትዝታለች!

አይጥ ድመት አሳብቃ በወጥመድ አስያዘችኝ ስትል፣ ድመት ደግሞ ለሷ የፃፍኩላትን ምላሽ ለጠላቴ (ለቤቱ ባለቤት) ሰጠችብኝ ትላለች፡፡ የቤቱ ባለቤት ደግሞ ስለምን እንደተፃፉም ሳያነብ ፍርድ ይሰጣል፡፡

ይህን የሆነውን ሁሉ ውሻ ቁጭ ብሎ ይታዘባል፡፡

“ወይ ግሩም! እነዚህ ፍጡሮች ሲሞቱም አይማማሩም!

ጠላት እንደሆኑ ኖረው ጠላት እንደሆኑ ሊሞቱ ነው፡፡ ጌታችንም፤

ጨካኝ ፍርደ -ገምድል ነው

በቀሉን ብቻ የሚያምን

በቋፍ በሥጋት የሚኖር

አንዱን ጥፋት ለማጥፋት፣ ሌላ ጥፋት የሚሠራ

ቁጥቋጦዎችን ለመንቀል፣ የሚጣላ ከተራራ…

ማንም ከማንም ላይሻል፣ ማንም ከማንም ላይበልጥ

አገር እንደበሬ ጠልፎ፣ ጥሎ ለመብላት መሯሯጥ

መንተፍተፍ…መተላለፍ፣ መጠላለፍ ሁሉን ማርገፍ!

ሁሉም መርገፍ!!” አለ፡፡

* * *

ከመጠላለፍ ይሰውረን፡፡ አደቡን ይስጠን፡፡ በተጠራጠርነው ሁሉ ፍርድ ከመስጠት ያድነን፡፡

እየደጋገምን የምናጠፋው ጥፋት እኛን ራሳችንን ይዞ እንዳይጠፋ መጠንቀቅ ያባት ነው! የምንገባው ቃል መፈፀሙን የሚያረጋግጥልን አንድም ታሪካችን፣ ሁለትም ለራስ መታመናችን ነው! በተግባር የምንሠራው በቃል የምናወራውን ካልመሰለ ዕቅዳችን፣ ስትራቴጂያችን ሁሉ፤ ውሃ የበላው ቤት እንደሚሆን አንርሳ! በታሪክ ያየነው ስህተት እንዳይደገም መጣጣር አዲስ ታሪክ መሥራት ነው!

“ታሪክ ራሱን ይደግማል” ፣ ይላል ታሪከኛው ሁሉ

እኔን ያሳሰበኝ ግና፡- ታሪክ በደገመ ቁጥር፤ ዋጋው እጅግ መቀጠሉ፤”ይለናል ሜይ ግሪንፊልድ፡፡ የሚያስከፍለን ዋጋ ብዙ ነው እንደ ማለት ነው፡፡

በርናርድ ሾው የተባለው ፀሐፊ “የአንዱ ሥጋ ለአንዱ መርዝ ነው፡፡ የአንዱ ዕድሜ ናፍቆት፤ የሌላው ዕድሜ መከፊያና ማዘኛ ነው! (one man’s meat is one man’s poison, one age’s longing another age’s loathing) የሚለው ይሄን ብጤውን ነው፡፡ የሚያስከፋን እየቀነሰ የሚናፍቀን የሚጨምርበትን ሁኔታ ለመፍጠር መደማመጥ፤ መግባባትና መተሳሰብ ያሻናል፡፡

ከፊል በእጅ፣ ከፊል በዲጂታል የሚከፈት ሠረገላ ቁልፍ (both manual and digital at the same time) ይዘን ለውጥ ማምጣት ከባድ ነው - ዘይትና ውሃ እንዲሉ፡፡ “ባለራዕይ-ለማኝ ዐባይ ሲገደብ የምሰጥህ ሁለት ብር አበድረኝ ይላል” እያሉ የአራዳ ልጆች እንደሚሳለቁት እንዳይሆን፤ በማንኛውም ረገድ ራስን መቻል እንደሚኖርብን ልብ እንበል፡፡ በምግብ ራሳችንን ችለን ረሀብተኛ ዲሞክራሲ ይዘን እንጓዝ ብንል የማያዋጣንን ያህል፤ በባዶ ሆድም ዲሞክራሲን አንግቦ መጓዝ ወንዝ አያሻግረንም፡፡ ጥቂት የናጠጡ ሀብታሞችና አያሌ የኔ-ብጤዎች ያሏት ሀገርም ሆነ ሰላሟን አጥታ ብዙ ሀብታሞችን ያፈራች ሀገር እንድትኖረን አይደለም ደፋ-ቀና የምንለው፡፡ እንደጥንቱ መፈክር “ጉዟችን ረጅም ትግላችን መራራ” ነው ማለትም አያዛልቀንም፡፡ ሁሌም ረጅም፣ ሁሌም መራራ መሆን የለበትምና! “ጊዜ ነው ይላል ሻጥረኛ፤ በጊዜ አሳቦ ሊተኛ!” ይለናል ፀጋዬ ገ/መድህን፡፡ “ሁሉ ነገር ሂደት ነው” በሚል መጠቅለያ ያለ ለውጥ፣ ያለ ዋስትና መራመድ አይቻልም፡፡ The change should be incremental እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ። የለውጥ አንቀሳቃሹ በአብዛኛው ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ነው፡፡ በዕውቀት የተገነባ፣ ለውጥ የገባው፣ ዛሬ ላይ የተደረሰው ብዙ ለውጥና መስዋዕትነት ታይቶ መሆኑን የተረዳ ወጣት እንጂ “Fast” በሚል ታርጋ የታሸገ የቢዝነስ ተሯሯጭ ለብ-ለብ ትውልድ ብቻ እንዳይሆን አገርና ነገር የገባው ወጣት መገንባት ያስፈልጋል፡፡ ያልፈጠርነውን፣ ያላስተማርነውን፣ በአግባቡ ያላነፅነውን ልጅ የሌለ ቅፅል ሰጥተን ብናሞካሸው ረብነት የለውም፡፡ በአናቱ ቅቤ ጣል ያለበት ሹሮ ዓይነት ካፒታሊዝም ኑሮአችን ቅቤ በቅቤ ነው እንደማያሰኝ ሁሉ፤ በእንዲህ ያለ ሥርዓት ውስጥ የሚያድግም ልጅ በአርቲፊሻል የተኳኳለ ከመሆን በቀር ኦርጅናሌ እንደማይሆን እናስተውል፡፡ “በወጉ ያላሳደገውን ልጅ የእከሌን ልጅ ይመስላል፤ ይላል” ማለት ይሄው ነው፡፡

የስፖርት ውድድርና የኪነጥበብ ዋጋ - በአየን ራንድ ፍልስፍና

ሕይወቱን የሚያፈቅር ሰው፣ ለሦስት ነገሮች ከሁሉም የላቀ ትልቅ ክብር መስጠት እንደሚገባው አየን ራንድ ስተምራለች። ከሁሉም የላቁ የተባሉት ሦስቱ እሴቶች እኚሁና፡ እውነታን አንጥሮ የሚገነዘብ የአእምሮ አስተውሎት (Reason)፣ የሕይወት አላማ (Purpose)፣ በራስ ብቃት መተማመን (selfesteem)። የኪነጥበብ ዋጋ እጅጉን  ልቅ የሆነው፤ እነዚህ እሴቶች ጎልተውና ጠርተው፣ በተጨባጭ ተቀርፀውና እውን ሆነው እንድናያቸው የሚያደርግ

ምናባዊ አለም ለመፍጠር ስለሚያስችል ነው። ሶስቱ የኪነጥበብ መሰረታዊ ባህርያትም፣ ከመሰረታዊዎቹ ሦስት እሴቶች ጋር (ከትኩረት፣ ከአላማ እና ከብቃት ጋር) የተሳሰሩ ናቸው። የኪነጥበብ ባሕርያት ከስፖርት ባሕርያት ጋር ምን ያህል እንደሚመሳሰሉ ተመልከቱ። 1. ኪነጥበብ፣ ዋና ዋና ቁም ነገሮችን ከትርኪምርኪ ለይቶና አጥርቶ ማሳየት ይችላል (selection and magnification)። ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ በአላስፈላጊ ነገሮች ላይ ሳይሆን በዋና ዋና ነገሮች ላይ እንድናተኩር ያደርጋል። ስለ ተጫዋቾች ችሎታ እንጂ ስለ ዘመዶቹ ቁጥር ወይም ስለ ጥርሱ ብዛት አናወራም። በቀጥታ የሚተላለፈው ውድድር ላይ፤ ተጫዋቾች ተቀባብለውና አብዶ ሰርተው ሲያልፉ፣ ኳስ ሲመቱና ጎል ሲያስገቡ ነው ማየት የምፈልገው? ወይስ የሜዳው የሳር ቅጠል ስፋትና ርዝመት፤ የተጨዋቹ ገምባሌ ስፌትና የክር አይነት ለ90 ደቂቃ ማየት እንፈልጋለን? ዋና ዋና ቁም ነገሮቹ ናቸው ጎልተው የሚወጡት። ከገምባሌ ስፌት ይልቅ የጎሉን አገባብ ለይቶ ያሳየናል፤ ደጋግሞም እንድናየው ያቀርብልና - አጥርቶ አጉልቶ። (selection and magnification) 2. ኪነጥበብ፤ ብቃትን በተጨባጭ ስጋና ደም አልብሶና በአርአያነት ሊጠቀስ የሚችል ጀግናን ቀርፆ ማሳየት ይችላል (concretization and model building)። ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ የሰውን ብቃት በእውን በተጨባጭ እንድናይ ያደርጋል። 3. ኪነጥበብ፤ የሩቁን አላማ በቅርበት እንድናጣጥመው የስኬት ጉዞውን አስተሳስሮ ማሳየት ይችላል (projection and recreation)። 

ምርጥ የስፖርት ውድድር፤ በትልቅና በከባድ አላማ እንዲሁ፤ በእልህ አስጨራሽ ትንቅንቅና ፉክክር ላይ የተመሰረ ነው - በዙር ጨዋታና በጥሎ ማለፍ ፉክክሩ ጦዞ በፍፃሜው ለዋንጫ ሲደረስ እናይበታለን። ምርጥ የስፖርት ውድድር እና ምርጥ ድራማ (ድርሰት) በጣም ተመሳሳይ ከመሆናቸው የተነሳ፤ ይዘታቸውም ይዛመዳል።

ገፀ ባሕርያትና ተጫዋቾች ስፖርታዊ ውድድር ደማቅና ማራኪ የሚሆንልን፤ በብቃት የገነኑና ከባድ አላማ የያዙ ተፎካካሪ ተጫዋቾች የሚታዩበት ከሆነ ነው።

ድርሰትም ውብ እና መሳጭ የሚሆንልን፤ በጀግንነት የገነኑና ፈታኝ አላማ የያዙ ተቀናቃኝ ገፀባሕርያትን መቅረፅ ሲችል ነው። በግጭት እየጦዘ የሚሄድ የድርጊት ሰንሰለት (ሴራ) ምርጥ ስፖርታዊ ውድድር ቁጭ ብድግ

የሚያሰኘን፤ ተጫዋቾች በእያንዳንዷ ደቂቃ አላማቸው ላይ አነጣጥረው የሚጣጣሩበት ታሪክ ስለምናይበት ነው። አታልሎ ማለፍ፣ ጎል ማስገባት፣ ማሸነፍ፣ ዋንጫ መውሰድ... የተጫዋቾቹ ድርጊት በሙሉ፣ ፉክክሩና ጥሎ ማለፉ ሁሉ እርስ በርስ የተሳሰሩ ናቸው። በአላማ ላይ ያነጣጠረ የፍልሚያ፣ የግጭት፣ የፉክክር መርሃ ግብር የምርጥ ስፖርታዊ ውድድር መለያ ነው - በግብግብ እየጦዘ የሚሄድ የውድድር ሰንሰለት (ሴራ) ልንለው እንችላለን።

ምርጥ ድርሰት ልብ ሰቅሎ የሚያጓጓን፤ ገፀባሕርያት በእያንዳንዷ ደቂቃ አላማቸው ላይ አተኩረው ሲታገሉ፣ ሲወጡና ሲወርዱ የሚያሳይ ታሪክ ስለሚያቀርብልን ነው። መውጪያ ወይም መግቢያ ቀዳዳ መፈለግ፣ ማምለጥ ወይም ማሳደድ፣ መያዝ ወይም ነፃ መውጣት... የገፀባሕርያቱ እንቅስቃሴ በሙሉ አላማን ለስኬት ለማብቃት

የሚደረግ ነው። ሁሉም ድርጊቶች የተሳሰሩ ናቸው - በአላማ ላይ ያነጣጠረ የትንቅንቅ፣ የግጭትና

የፉክክር ታሪክ ነው - በግጭት እየጦዘ የሚሄድ የድርጊት ሰንሰለት (ሴራ)። የአቀራረብ ዘይቤ (ስታይል)

የስፖርታዊ ውድድሮች አቀራረብ በአዘጋጆቹ መንፈስና ዝንባሌ ይለያይ የለ? በድርሰትም እንደዚያው ነው። የሁለት ድርሰቶች ታሪክ ተመሳሳይ ቢሆን እንኳ እንደደራሲዎቹ መንፈስ አቀራረባቸው ሊለያይ ይችላል። የአንዱ ደራሲ የአቀራረብ መንፈስ (ስታይል) እንደ አፍሪካ ዋንጫ በወግ የደበዘዘ በጥሬ ስሜት የተንዘፈዘፈ ይሆናል። የሌላኛው

ደራሲ ስታይ ደግሞ፣ እንደ አሜሪካ የቅርጫት ኳስ ዋንጫ ያሸበረቀና የተሽቀረቀረ ይሆናል። የአንዱ

ደራሲ፤ እንደ ጀርመኑ ቡንደስ ሊጋ ቆጠብ ደደር ያለ፤ የሌላኛው እንደ እንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ የተጯጯኸና የተቀወጠ። ስፖርታዊ ወድድርና ድርሰት፣ ሌላ ተመሳሳይ ተፈጥሮ አላቸው። ሁለቱም፤ በቅጡ የሚታወቅ ጭብጥ (ጥቅል ሃሳብ) ሊኖራቸው ይገባል። ጭብጥ፡ የምን ጨዋታ የምን ድርሰት? ስለተጫዋቾችም ሆነ ስለ ዋንጫ፤ ስለ ጥሎ ማለፍም ሆነ ስለ ፉክክሩ ጡዘት፣ አልያም ስለውድድሩ የአቀራረብ መንፈስ መነጋገር የምንችለው፤ በቅድሚያ የውድድሩን ምንነት ስናውቅ ነው። በአጭሩ የውድድሩ ይዘት፣ ሂደትና

አቀራርብ፤ በውድድሩ ምንነት ላይ የተመሰረተ መሆን ይገባዋል። “የ2013 የአፍሪካ እግርኳስ ዋንጫ”፣ “የ2012 ኦሊምፒክ”፣ “የ2014 የአለምአትሌቲክስ ሻምፒዮና”፣ “የሰፈር ልጆች የእግር ኳስ ግጥሚያ”፣ “የባለስልጣናትና የነጋዴዎች የእግር ኳስ ጨዋታ”... እነዚህ ሁሉ አንድ አይነት ይዘት ወይም አቀራረብ ሊኖራቸው አይችልም። የውድድሩን ጭብጥ ለይተን በጥቅሉ ስናውቅ ነው፤ ምን አይነት ተጫዋቾችና ዋንጫ፣ ምን አይነት ትንቅንቅና

የውድድር መርሃ ግብር እንደሚኖር በአጠቃላይ የውድድሩ ይዘትና ሂደት ምን መምሰል እንዳለበት

መምረጥና መወሰን የሚቻለው። የውድድሩ ይዘት፤ ሂደትና አቀራረብ፤ በውድድሩ ጭብጥ ይወሰናል

ማለት ነው። የወዳጅነት ወይም የእርዳታ ማሰባሰቢያ ውድድርንና የአለም ዋንጫንና ኦሊምፒክን በአንድ አይነት መንፈስ ማቅረብ አይቻልም፤ ውድድሮቹና ተጫዋቾቹም ይለያያሉ።

 

በድርሰትም እንዲሁ፤ ገፀባሕርያቱንና አላማቸውን፣ ግጭቱንና ሴራውን ለመምረጥና ለመወሰን፣ በቅድሚያ ደራሲው በምን ዙሪያ ለመፃፍ እንደሚፈልግ ጭብጡን ለይቶ ማወቅ ይጠበቅበታል። ለምሳሌ የዴርቶጋዳ ጭብጥ፤ “በጥንታዊ መሰረት ላይ ለኢትዮጵያ ትንሳኤ የሚባትሉ ዜጎች” የሚል ነው። “የሰዎችን ህይወት የሚያሰናክልና የሚያዋርድ ኋላቀር ህብረተሰብ ውስጥ የሚኖሩ ሚስኪን ፍቅረኞች” ... ይሄ ደግሞ የፍቅር እስከ መቃብር ጭብጥ ነው። “ድሆችን የሚበድል ፍትህ የተጓደለበት ስርዓት ውስጥ የሚኖር ጀግና” ... ዘ ሚዘረብልስ የተሰኘ መፅሃፍ። “አገርን የሚዋጅና ፍትህን የሚፈፅሙ ጀብደኞች” ... ዘ ስሪ ማስከቲርስ። “ፍቅሩንና ነፃነቱን ተቀምቶ ፈተና ውስጥ የገባ ቅን ሰው” ... ዘ ፍዩጀቲቭ የተሰኘ ፊልም። የጭብጡ ስፋትም ሆነ ጥልቀት የደራሲው ምርጫ ነው። ቅልብጭ ያለ እና የሾለ ሊሆን ይችላል። የእውቀቱንና የአቅሙን ያህል የሚመጥን፣ የዝንባሌውንና የፍላጎቱን አዝማሚያ የሚጣጣም መሆን አለበት።

ከላይ እንደተጠቀሰው፤ የድርሰት ዋና አላባዊያን 1. ጭብጥ፣ 2. የገፀባሕርያት አሳሳል (አላማን ጨምሮ)፣ 3. ሴራ (ግጭትን ጨምሮ)፣ 4. የአቀራረብ ዘይቤ (ስታይል) ናቸው። በስፖርታዊ ውድድርም ውስጥ፤ አላባዊያኑ ተመሳሳይ ናቸው። እስቲ በገፀባሕርያት አሳሳልና በሴራ ላይ በማተኮር ተመሳሳይነታቸውን በደንብ ለመመልከት እንሞክር።

የገፀ ባሕርያት አሳሳል፡

ከ31 አመት በኋላ ወደ አፍሪካ ዋንጫ የተመለሰ፤ ባለፈው የአፍሪካ ዋንጫ የወሰደ፤ በማጣሪያው ያለፈ፤ በፕሮፌሽናል ተጫዋቾች የተገነባ፣ በውዝግብ የተበጠበጠ፤ በሽልማት ቃል የተገባለት፣ ብዙ ፈተና ያለበት ... የቡድን አወቃቀርና አመራር፣ የስፖርተኞች ብቃትና ዝግጅት፣ የአሰልጣኝ ብቃትና ዝግጅት ... ዋና ዋና ነገሮች ላይ ማተኮር። ለምሳሌ የፊዚክስ ሳይንቲስት፣ የአውሮፕላን ኢንጂነር፣ የአንጎል ሃኪም፣ የፋብሪካ ምርጥ ማኔጀር፣ የቢዝነስ ጥበበኛ፣ ምርጥ አልሞ ተኳሽ .... ላይ አናተኩርም። በዘመድ፣ በጓደኝነት፣ በጉቦ፣ በእጣ፣ በሃይማኖት ተከታይነት፣ በብሄረሰብ፣ ... አጓጉል ሃሳቦችን አናመጣም። በጉዳይህ ላይ ዋና ዋና ነገሮችን ለይቶ ማወቅና እነሱን በትኩረት ማስተዋል... የተዘበራረቀ፣ የተንሸዋረረ፣ የዘፈቀደ፣ የፈዘዘ፣ የደነዘዘ፣ የተደናበረ አስተሳሰብ እንዳይኖረን ያደርጋል።

የተወዳዳሪ ቡድኖች፣ የአሰልጣኞች፣ የተወዳዳሪዎች ... ማንነት፣ አላማ፣ ብቃት፣ አቅም፣ ዝንባሌ... የተወሰነ መረጃ “ከኤክስፖዚሽን” እናገኛለን። እንግዲህ የስፖርታዊ ውድድር ኤክስፖዚሽን የሚቀርበው፤ በማጣሪያ ውድድሮች ላይ፣ በዝግጅትና በልምምድ ወቅት፣ እንዲሁም በሚዲያ ዘገባዎች አማካኝነት ነው። የገፀባሕርያቱ ማንነት እየጎላ የሚመጣውና እየጠራ የሚታየን ግን... ታሪኩ ከጀመረ በኋላ ወይም በግጭት የተወጠረ የድርጊት ሰንሰለት ውስጥ (ሴራው ውስጥ) ነው። የተጨዋቾቹ ማንነትና ብቃት በግላጭ የምናየውም፤ ጨዋታው ከጀመረ በኋላ በትንቅንቅ የከረረ በውድድሩ ሂደት ውስጥ (በሴራው ሰንሰለት ውስጥ) ነው። ይሄኔ መሪውና ተቀናቃኝ ፍንትው ብለው ይወጣሉ። የገፀባሕርያቱ ልዩ መልክ ነጥሮ ይወጣል - ዋና መሪ ገፀባሕርይ፣ ዋና ተቀናቃኝ ገፀባሕርይ፣ ደጋፊ ገፀባሕርያት፣ እኩይ ገፀባሕርያት...

እንደ ጥሩ ድርሰት ሁሉ፤ ጥሩ ስፖርታዊ ውድድርም ቢያንስ ሁለት ጀግና ገፀባሕርያት (ጠንካራ ተፎካካሪዎች) ያስፈልጉታል። ነገር ግን፣ ጀግኖቹ እንደ የብቃታቸውና እንደ የዝንባሌያቸው፤ አላማቸውን ለማሳካት የሚመርጡት መንገድ ይለያያል። መጥፎ ነገር የመስራት አባዜ አልተጠናወታቸውም። ግን፤ አንዱ በፅናት ትክክለኛውን መንገድ የሚከተል፣ ሌላኛው ግን አንዳንዴ ወደ ስህተት ለመግባት የሚቃጣው ሊሆን ይችላል - ለምሳሌ ሰዓት ማባከንና ተጠለፍኩ ብሎ የውሸት መውደቅ። ቢሆንም፤ በጨዋታው ህግ እየተዳኙ የሚጫወቱ ናቸው። ሜዳ ውስጥ የገቡት፣ በሰዓት ማባከን ችሎታ ወይም ተጠለፍኩ ብሎ ዳኛ በማታለል ጥበባቸው አይደለም። የእግር ኳስ ብቃታቸውና ጥረታቸው ነው ዋናው ነገር። ዋና አላማቸውም ማታለልና ማሰናከር አይደለም። ዋና አላማቸው ተጫውቶ ማሸነፍ ነው። የተለያዩ ጉድለቶች ቢኖሯቸውም፣ በጥቅሉ ጀግኖች ናቸው። እንደየጉድለታቸው መጠንም ችግር ይገጥማቸዋል።

1. ዋናው መሪ ገፀባሕርይ (ፕሮታጎኒስት)፡ እንግዲህ በላቀ ብቃትና በጥሩ ጨዋታ እያሸነፈ ዋንጫ ለመውሰድ ቆርጦ የተነሳ ነው ዋናው መሪ ገፀባሕርይ። በምርጥ አጥቂዎች ላይ የተገነባ ቡድን ነው እንበል። (ከድርሰት አለም ውስጥ አንድ ሁለት ፕሮታጎኒስቶችን ብንጠቅስስ? ለምሳሌ የባንክ ዘራፊውን አሳድዶ ለመያዝ የሚፈልግ ፖሊስ፣ ወይም ፍቅረኛውን ከአጋቾች ለማዳን የሚፈልግ እጮኛ)

2. ዋናው ተቀናቃኝ ገፀባሕርይ (አንታጎኒስት)፡ የተወሰኑ ጉድለቶች እንዳሉት በማመን በመከላከል ላይ አተኩሮ ለማሸነፍ በእልህ የሚጫወት ቡድን ሊሆን ይችላል። (በድርሰቱ አለም ደግሞ፤ የባንክ ዘራፊውን ለመያዝ ግብረአበሮቹን ማግባባት አለብን የሚል ፖሊስ፤ አልያም ከአጋቾቹ ጋር በመደራደር ታጋቿን ለማስለቀቅ የሚጣጣር አባት...)

ተጨማሪ ገፀባህርያት

1. ደጋፊ ገፀባሕርያት፡ ዳኞች፣ አሰልጣኞች፣ ተመልካቾች፣ አድናቂዎች፣ ጋዜጠኞች፣ ሸላሚዎች...

2. እኩይ ገፀባሕርያት (ቪሌይን)፡ ተሳዳቢ ቲፎዞ፣ አድሏዊ ዳኛ፣ የሚያዛባ ጋዜጠኛ፣ የቁማር ማፊያ፣ በዘርና በአገር ተቧድኖ ውድድሩን የሚበጠብጥ ጋጠወጥ፣ ኳስ መጫወትም ሆነ ማየት የለባችሁም የሚል አክራሪ፣ ከኳስ ደስታ ይልቅ ለችግረኞች ሃዘኔታ ቅድሚያ እንስጥ የሚል ዘመነኛ ባህታዊ... ወዘተ

ጠንካራ ሴራ፡ የጀግኖች ግጭት

ሁለቱ ጀግና ገፀባሕርያት (በወኔ የታነፀው ፖሊስና ትእግስት የተላበሰው ባልደረባው) አላማቸው ተመሳሳይ ቢሆንም ተቀናቃኝ መሆናቸው አይቀርም። ሁለቱም ጀግኖች ስለሆኑም ግጭታቸው ጠንካራ ይሆናል - (የፍፃሜ ውድድር ላይ እንደሚገናኙ ተፎካካሪ ቡድኖች ማለት ነው)።

ለምሳሌ ዘ ሚዘረብልስ የተሰኘው የቪክቶር ሁጎን ድርሰት መጥቀስ ይቻላል። ዋናው ገፀባሕርይ ፍትሕ ለማግኘት የሚታትር ነው። ተቀናቃኙ ደግሞ፣ ህግ መከበር አለበት ይላል - ዣቬር። ለያዙት አላማ ፅኑ ናቸው፤ ብቃታቸውን ተጠቅመው ይፋጫሉ። ዣቬር ባይኖር የዣን ቫልዣ ታሪክ ይኮሰምናል። ጠንካራ ተፎካካሪ እንደሌለው የፍፃሜ ውድድር፤ እርባና ቢስ ታሪክ ይሆናል።

ታዲያ በሁለቱ ጀግኖች ግጭት መሃል፤ ዣን ቫልዣን እንደ አባት የምትወደው ወጣት ሴት አለች። ይህችን ሴት በመጠቀም ዣን ቫልዣን ለመዝረፍና ለመጉዳት የሚፈልጉ መናኛ እኩይ ገፀባህርያትም ይኖራሉ። ግን የዣን ቫልዣ ትንቅንቅ ከመናኛና ከእኩይ ገፀባሕርያት ጋር አይደለም። ከጠንካራውና ከጀግናው ዣቬር ጋር ነው ትግሉ። ድርሰቱ ከምዕተ አመት በኋላም እግጅ ተወዳጅ ታሪክ ለመሆን የበቃበት ትልቁ ሚስጥር ይሄው ነው።።

ከዘመኑ ፊልሞችም አንድ ምሳሌ መጥቀስ ይቻላል - ሃሪሰን ፎርድ የሚሰራበት ዘ ፊጁቲቭ የተሰኘው ፊልም። ሚስትህን ገድለሃል ተብሎ በሃሰት የተፈረደበት ሃኪም ከእስር ሲያመልጥ ነው ታሪኩ የሚጀምረው። ሚስቱን የገደሉበትና በተንኮል ለእስር የዳረጉትን ሰዎች አጋልጦ ንፁህነቱን ሳያስመሰክር ወደ እስር መመለስ አይፈልግም። ይህን አላማ ማሳካት አለበት። ኮምጫጫው ህግ አስከባሪ ደግሞ፤ ከእስር ያመለጡ ሰዎችን የገቡበት ገብቶ መያዝና ማሰር ስራው ነው። ህግ መከበር አለበት ባይ ነው። የሁለቱም አላማ ትክክል ነው፤ ፅናት አላቸው። አላማቸውን የሚያሳኩበት ብቃትና ብርታት አላቸው። ፍጭቱ ሃይለኛ ነው። ፊልሙ ደግሞ እጅግ መሳጭ ታሪክ።

መናኛዎቹ እኩይ ገፀባሕርያት፣ በራሳቸው አቅም የታሪኩን አቅጣጫ የመቀየር አቅም የላቸው - ጀግኖቹ ገፀባሕርያት ደካማ ካልሆኑና ካልፈቀዱላቸው በቀር። የጀግኖቹ ግጭት ተባብሶና ጦዞ እልባት ላይ ሲደርስ፤ እኩዮቹ ገፀባሕርያት እርቃናቸውን ይቀራሉ። በእግር ኳስ ውድድርም ተመሳሳይ ነው። ጨዋታው የሚያምረው፣ ከፍተኛ ብቃት ባላቸው ምርጥ ተጫዋቾች ሲወዳደሩ ነው።

ሦስቱ የኪነጥበብ ባሕርያት ሲጓደሉ

ዋና ዋና ነገሮች ላይ አለማተኮር ማለት ምን ማለት እንደሆነ ለመገንዘብ ምሳሌዎችን ልጥቀስላችሁ። ያህል ይሉሃል ይሄ ነው። የተፈነከተ ተመልካች ላይ የሚደረግ የረቀቀ ህክምና ስናይ ብንውል? አጥቂው እያታለለ ሲያልፍ ለአፍታ አሳይቶ ከዚያ በኋላ ለ10 ደቂቃ ያህል የሜዳውን የሳር ቅጠል ብዛትና ስፋት ከተለያየ አቅጣጫ እየቀረፀ ቢያሳየንስ? አንድ ሁለት ተቀባብለው፣ ወደ ግራ ክንፍ አሻግረው፣ ወደ ግብ... ካሜራው ይህንን አቋርጦ ጨዋታው እስኪያልቅ ድረስ የተጨዋቹ የገምባሌ ስፌት እና የፀጉሩ ቀለም ከተለያየ አቅጣጫ እየደጋገመ ቢያሳየንስ? በቲቪ በቀጥታ የሚተላለፈው ጨዋታው ሳይሆን፤ የአሰልጣኞችን ክርክርና ዛቻ ወይም የተጫዋቾችን ተረብና የቅፅል ስም አጠራር ቢሆንስ? ወይም፤ በትንታኔና በቲዎሪ ፉክክር ብቻ ነገሩ ቢጠናቀቅስ? ተጨባጭ ታሪክ ሳይኖረው፤ በገለፃና በትንታኔ የታጨቀ ድርሰትም፤ ከሬድዮ ቶክ ሾው የተሻለ ዋጋ አይኖረውም።

ብቃት የማያስፈልገው ውድድር ቢሆንና ማጣሪያና ምርጫ ባይኖርስ? ለምሳሌ በእጣ ሊሆን ይችላል። እግር ኳስ ማየት፤ የሎተሪ እጣ ሲወጣ ከማየት የተለየ አይሆንም ነበር። የተጫዋቾችን ብቃት መመዘን ባንችል ኖሮስ? ስለ ቼዝ የማናውቅ ከሆነ የቼዝ ጨዋታ ለማየት እንጓጓም። ምክንያቱም የተጨዋቾችን ብቃት መመዘን አንችልም። ማሸነፍና ዋንጫ ማግኘት የሚቻለው በእርዳታ ቢሆንስ ኖሮ? አንዱ ቡድን በባዶ እግር በአምስት ሰው ብቻ እንዲጫወት የሚፈረድበት ቢሆን?ተጫዋቾች በብቃታቸው የማይመረጡ ቢሆንስ? ስማቸው በ”ኤ” የሚጀምርና በውድቅት ሌሊት የተወለዱ ብቻ የሚካፈሉበት ውድድር ቢሆንስ? ብቃትን አጉልቶ የማያወጣ ውድድር፤ ከንቱ ልፊያ ይሆናል። ይህ ነው የሚባል ብቃት በሌላቸው ገፀባሕርያት የታጨቀ ድርሰትም እንደዚያው ነው።

ግብ እና ዋንጫ ባይኖርስ? (7 ቁጥሩ ለ9 አሳለፈ፣ ጠለዘ፣ ነዳ ... ይህንን ለስንት ደቂቃ ሳይሰለቸን ማየት እንችላለን? አሸናፊው ተለይቶ የሚታወቀው በቲፎዞ ብዛት ቢሆንስ? ጎል ሲያገባ እንደ ዳኛው ፍላጎት፣ ለሌኛው ቡድን ነጥብ ቢሰጥስ? ለማሸነፍ ባይጫወቱስ? በይሉኝታ መሸነፍ፣ ለሌላው አዝኖ ራስን መስዋዕት ማድረግ፣ ያሸነፈ ቡድን ራስ ወዳድ ተብሎ ቢወገዝስ? የዘንድሮው ሻምፒዮና፣ በስህተት በራሱ ላይ ብዙ ግብ ያስቆጠረ ቡድን ነው ቢባልስ?