Administrator

Administrator

የትግራይ ክልል ጊዜያዊ አስተዳደር ፕሬዚዳንት አቶ ጌታቸው ረዳ፤ “በትግራይ ክልል የሚፈጠረው ችግር ኢትዮጵያን የማተራመስ አቅም አለው” በማለት ተናግረዋል። ፕሬዚዳንቱ የፌደራል መንግሥቱ ለጊዜያዊ አስተዳደሩ ደጋፍ መስጠት አለበት ብለዋል፡፡
ዛሬ በሸራተን አዲስ ሆቴል ለጋዜጠኞች መግለጫ የሰጡት አቶ ጌታቸው ረዳ፤ የትግራይ ክልልን ወቅታዊ ሁኔታ በተመለከተ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ሰጥተዋል። ፕሬዚዳንቱ፣ "የእኔ ፍላጎት ጦርነትን ማስወገድ ነው፡፡ ሌላ ጦርነት ማካሄድ ሳይሆን ጦርነትን ለማስወገድ የሚያስችሉ ሁሉም አስፈላጊ እርምጃዎች መወሰድ አለባቸው” ሲሉም ተደምጠዋል።
"እዚህ ውስጥ የእርስ በርስ ግጭትን ማስቀረት መቻል ስላለብን፣ እንዲሁም ሌሎች ጠላቶች ገብተው ይሄን ሊጠቀሙበት የሚችሉበትን ዕድልም መከልከል ስላለበት፣ ፌደራል መንግስት ለዚህ ‘በቂ ነው’ የሚለውን ድጋፍ መስጠት ‘አለበት’ የሚል ዕምነት አለኝ" ያሉት አቶ ጌታቸው፤ በትግራይ ክልል የሚፈጠረው ችግር ኢትዮጵያን የማተራመስ አቅም እንዳለው ጠቅሰዋል። አክለውም፤ “ከኤርትራ ጋር ግንኙነት መፍጠር ካስፈለገ፣ የተፈጸሙትን ጭፍጨፋዎች በመካድ አይደለም የሚፈጠረው” ብለዋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ በዛሬ መግለጫቸው፤ የፕሪቶሪያ ስምምነትን ለማፍረስ “እየተደረገ ነው” ያሉት እንቅስቃሴ በፍጥነት እንዲገታም ጥሪ አቅርበዋል።
የአፍሪካ ወጣቶች የሮቦቲክስ ፈጠራ ችሎታቸውን የሚያሳዩበት 3ኛው የአፍሪካ ሮቦቲክስ ሻምፒዮንሺፕ ውድድር ዛሬ በአዲስ አበባ ሳይንስ ሙዚየም በታላቅ ድምቀት ተከፍቷል።
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ዶክተር ባይሳ በዳዳ በመክፈቻው ላይ ባደረጉት ንግግር፤ "የአፍሪካ ሮቦቲክስ ሻምፒዮንሺፕ ውድድር ኢትዮጵያን ከድህነት ለማላቀቅ፣ ታዳጊዎችን በቴክኖሎጂ ለማብቃት ወሳኝ ምዕራፍ ነው" ብለዋል። ሚኒስቴር መስሪያ ቤታቸው ለወጣቶች የቴክኖሎጂ ክህሎት እድገት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ቃል ገብተዋል።
የኢትዮ ሮቦቲክስ መሥራችና ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰናይክረም መኮንን በበኩላቸው፤"ከዛሬ መጋቢት 4 እስከ 6 ቀን 2017 ዓ.ም ለሦስት ቀናት በሚካሄደው በዚህ ውድድር ላይ የመጀመሪያ ደረጃ፣ የሁለተኛ ደረጃ፣ የኮሌጅና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች በፈጠራ ችሎታቸው ይወዳደራሉ፤ ውድድሩም በዲዛይን፣ በኢንጂነሪንግና በአውቶኖሚ ኮዲንግ ላይ ያተኩራል" ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የውድድሩ ዓላማ ወጣቶች በቴክኖሎጂ ዘርፍ ያላቸውን ክህሎት ማዳበርና ማበረታታት እንዲሁም በዓለም አቀፍ ደረጃ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ማድረግ ነው ያሉት አቶ ሰናይክረም፤ የውድድሩ አሸናፊዎች የዋንጫ ሽልማትና ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የተፈረመ የምስክር ወረቀት ይበረከትላቸዋል ብለዋል፡፡
ዋና ሥራ አስኪያጁ አክለውም፤ "እንደ አህጉር መጪውን ትውልድ የሚያጎለብት የዲጂታል ቴክኖሎጂና የምህንድስና ትምህርት ባህል መፍጠር ላይ ማተኮር አለብን" ሲሉ ተናግረዋል፡፡
የውድድሩ አሸናፊዎች ከነገ በስቲያ ቅዳሜ ይፋ የሚደረጉ ሲሆን፤ ለፍጻሜ የሚበቁ ተማሪዎች አገራቸውን ወክለው በአሜሪካ በሚካሄደው ዓለም አቀፍ የሮቦቲክስ ውድድር ላይ ይሳተፋሉ ተብሏል፡፡

ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ከዩኤን ውመን ጋር የሴቶች ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚነትን ለማረጋገጥ “ይረዳል” የተባለለትን የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል። በባንኮች ላይ በአመራርነት የሚሰሩ ሴቶች ቁጥር አነስተኛ ስለመሆኑም ተገልጿል።

ዛሬ መጋቢት 4 ቀን 2017 ዓ.ም. በሒልተን ሆቴል በተካሄደው የውይይት መድረክ ላይ የዩኤን ውመን የኢትዮጵያ ተወካይ ሲሲል ሙካሩባጋን ጨምሮ፣ ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው ዕንግዶች ተገኝተዋል። በመድረኩ ሴት ስራ ፈጣሪዎች ከመነሻ ካፒታል እና ሌሎች የፋይናንስ አገልግሎቶችን ከማግኘት አንጻር የተለያዩ ፈተናዎች እንደሚገጥማቸው ተጠቅሷል።

ባለፉት 30 ዓመታት ውስጥ በሴቶች አቅም ግንባታ፣ ዕኩል ተጠቃሚነት እና ተያያዥ ጉዳዮች ዙሪያ ከፍተኛ ስራዎች እንደተሰሩ ተገልጿል። ይሁንና ቀላል የማይባሉ ተግዳሮቶች ሴቶች በስራ ፈጠራ እና ኢኮሚያዊ ተሳትፎ ላይ ጠንክረው እንዳይወጡ እንዳደረጋቸው ተነግሯል።

በመድረኩ ላይ ከቀረበው ገለጻ ለመረዳት እንደተቻለው፣ በኢትዮጵያ ያሉ የፋይናንስ ተቋማት ለሴቶች ብድር የሚሰጡት ከ13 በመቶ ባነሰ መጠን ነው። ይህም ከወንዶች እንጻር ሲመዘን “አናሳ ነው” ተብሏል።

በተጨማሪም፣ አሁን በስራ ላይ በሚገኙ ባንኮች ላይ በሃላፊነት እየሰሩ ያሉ ሴቶች 12 ነጥብ 5 በመቶ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ ይህም ብሔራዊ ባንክ ካስቀመጠው የሴት ሃላፊዎችን ብዛት ከወንድ አቻዎቻቸው አንጻር 25 በመቶ ገደማ እንዲደርስ ካስቀመጠው ግብ አንጻር አናሳ መሆኑን ተጠቁሟል።

በዚህም ተጨባጭ ዕምርታዎችን የሚያሳዩ ስራዎች መስራት እንደሚያስፈልግ ተጠቅሷል። እንዲሁም ሴቶች የኢኮኖሚ አቅማቸውን ካጠናከሩ፣ አጠቃላይ መብቶቻቸውን ማስጠበቅ “ይችላሉ” ተብሏል።

ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በሚተገብራቸው፣ በተለይ ሴቶችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ፕሮጀክቶችን አስመልክቶ አቶ በግዱ ሃይለመስቀል የዳሰሳ ጥናት አቅርበዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ፣ ባንኩ ከUN Women ጋር የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርሟል።

የሴቶችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ “ይረዳል” የተባለለት ይህ የመግባቢያ ሰነድ በባንኩ የዓለም አቀፍ ባንክ አገልግሎት ምክትል ቺፍ ኦፊሰር ወይዘሮ ሐረገወይን አምሳለ እና በUN Women የኢትዮጵያ ተወካይ ሲሲል ሙካሩባጋ አማካይነት ተፈርሟል።

• 2.5 ሚሊዮን ብር ፈጅቷል ተብሏል

በአጠቃላይ 2.5 ሚሊዮን ብር እንደፈጀ የተነገረለት "እንግዱ" የተሰኘ ልብ አንጠልጣይ ትሪለር ይዘት ያለው አዲስ ፊልም፣ ከመጋቢት 5 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ እንደሚመረቅ ተገለጸ፡፡

በሳዳም ነጌሶ ተደርሶ ዳይሬክት የተደረገው ፊልሙ፤ በልባም ፒክቸርስ ተዘጋጅቶ በሳዳም ፊልም ፕሮዳክሽንና በሶሎዳ ስቱዲዮ መቅረቡ የተነገረ ሲሆን፤ የ1 ሰዓት ከ32 ደቂቃ እርዝማኔ ያለው ነው ተብሏል፡፡

ዛሬ ጠዋት ረፋዱ ላይ በፊልሙ ዙሪያ ፕሮዲዩሰሮቹና ተዋናዮቹ በሪፌንቲ ሞል (ቦሌ ቡልቡላ) ለሚዲያ ባለሙያዎች ጋዜጣዊ መግለጫ በጋራ ሰጥተዋል፡፡

"እንግዱ" የተሰኘውን ፊልም ሰርቶ ለማጠናቀቅ ከ8 ወር በላይ እንደፈጀ የተገለጸ ሲሆን፤ በፊልሙ ላይ ከ35 በላይ ታዋቂና አጃቢ ተዋናዮች እንደተሳተፉበት ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከፊልሙ መሪ ተዋናዮች መካከል፡- አንጋፋው ተዋናይ ሰለሞን ሙሄ፣ ኤደን ገነት፣ ታዋቂው ኮሜዲያን ደረጄ ሀይሌ፣ ጌዲዮን ፍቃዱና አሰፋ ገ/ሚካኤል ይገኙበታል፡፡

የፊልሙ ቀረጻ እዚሁ አዲስ አበባ የተከናወነ ሲሆን፤ ከ65 በመቶ በላይ በሪፌንቲ ሞል ህንጻ ላይ መቀረጹ ተነግሯል፡፡

እንግዱ የተባለው ገጸባህርይ 7 ዓይነት ማንነቶችን ወይም ሰብዕናዎችን የያዘ መሆኑ ፊልሙን ለየት ያደርገዋል ያለው ደራሲና ዳይሬክተሩ ሳዳም ነጌሶ፤ የዚህን መነሻ ሃሳብ የወሰደው እ.ኤ.አ በ2016 ዓ.ም ከተሰራው Split የተሰኘ የሆሊውድ አስፈሪ ትሪለር ፊልም መሆኑን ጠቁሟል፡፡

በፊልሙ ላይ እንግዱን ሆኖ የተወነው ጌዲዮን ፍቃዱ በሰጠው አስተያየት፤ "ስክሪፕቱን ለመጀመሪያ ጊዜ ሳነበው ልሰራው የማልችለው ነበር የመሰለኝ፡፡ በአንደ ሰው ላይ ሰባትና ከዚያ በላይ ማንነቶችን ማሳየት ፈታኝ ነበር፡፡ እንደምንም ግን ተወጥቼዋለሁ" ብሏል፡፡

"እንግዱ" ፊልም በትላንትናው ዕለት በዓለም ሲኒማ ለአርቲስቶችና ለፊልሙ ቤተሰቦች ለዕይታ የበቃ ሲሆን፤ መጋቢት 5, 6 እና 7 እንዲሁም መጋቢት 12, 13 እና 14 ቀን 2017 ዓ.ም በሁሉም ሲኒማ ቤቶች በይፋ እንደሚመረቅ ታውቋል፡፡

ኦክሎክ ሞተርስና አንዳንድ ማህበራት በመካከላቸው ተፈጥሮ የነበረውን አለመግባባት በእርቅ መፍታታቸውን አስታውቀዋል፡፡

ይሄ ይፋ የተደረገው ዛሬ ጠዋት ረፋድ ላይ የኦክሎክ ሞተርስ ሥራ አስኪያጅ፣ እንዲሁም የሽማግሌና የማህበራቱ ተወካዮች በተገኙበት በድርጅቱ ዋና መ/ቤት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ ነው፡፡

ኦክሎክ ሞተርስ ባሰራጨው መግለጫ እንዳመለከተው፤ ከጥቂት ወራት በፊት በተሳሳተ መረጃና ጉዳዩን በጥልቀት ካለመረዳት የተነሳ ከድርጅታችን ጋር የሽያጭ ውል በመግባት ተሽከርካሪዎችን ለመግዛት ተስማምተን በጋራ እየሰራን ካሉ በርካታ ማህበራት ውስጥ በተወሰኑ ማህበራትና ግለሰቦች አማካኝነት በድርጅቱ ላይ የስም ማጥፋት ተግባር ተፈፅሞ ነበር፡፡

ይሁን እንጂ ማህበራቱና አባላቱ ጉዳዩን በጥልቀት ከመረመሩና በጊዜው የተነገራቸውን መረጃዎች መለስ ብለው በማጣራትና ከድርጅታችን ጋር በመነጋገር፣ በሀገራችን ባህል ወግ መሰረት፣ ችግሩን በእርቅ ፈተን በመስማማት ወደ ትግበራ ስራ ገብተናል ብሏል፤ ድርጅቱ በመግለጫው።

ኦክሎክ ሞተርስና ማህበራቱን በሽምግልና ለማስታረቅ እልህ አስጨራሽ ጥረት መደረጉ የተገለጸ ሲሆን፤ የማታ ማታ ስምምነት ላይ መደረሱ ይፋ ተደርጓል፡፡ በዚህም መሰረት ገንዘብ የሚፈልጉ ገንዘብ፣ መኪና የሚፈልጉ ገንዘብ እንዲወስዱ የተስማሙ ሲሆን፤ በዛሬው ዕለት 20 ያህል አባላት መኪና እንደሚረከቡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ገንዘብ የሚፈልጉ ደግሞ በ45 ቀናት ውስጥ ገንዘባቸውን እንደሚወስዱ ተነግሯል፡፡

በእርቅ ስምምነት ላይ የደረሱት የማህበራት ተወካዮች በሰጡት አስተያየት፤ "ወደ ህግ መሄድ ጊዜ የሚፈጅና አላስፈላጊ ወጪ የሚያስከትል በመሆኑ ችግራችንን በእርቅ ለመፍታት ተስማምተናል" ብለዋል፡፡

በኦክሎክና ማህበራቱ መካከል እርቅ ለማድረግ ተነሳሽነቱን የወሰዱት የሽማግሌዎቹ ተወካይ እንደገለጹት፤ መጀመሪያ ላይ ከሁለቱም ወገኖች ተቀባይነት አላገኙም ነበር፡፡ "በተለይ ማህበራቱ ከኦክሎክ የተላክን መስሏቸው ዕርቁን አሻፈረን ብለው ነበር፤ ዓላማችን በሁለቱ መካከል ሰላምና እርቅ መፍጠር መሆኑን ካረጋገጡ በኋላ ነው የተስማሙት" ብለዋል፤ በሰጡት መግለጫ፡፡

የኦክሎክ ሞተርስ ሥራ አስኪያጅ አቶ ታመነ ካሣሁን በበኩላቸው፣ መጀመሪያ ላይ በማህበራቱ በኩል ስለድርጅቱ የተሳሳተ መረጃ ይሰራጭ እንደነበር አንስተዋል፡፡ ለአብነት ያህልም፡- ኦክሎክ ከማህበራቱ አባላት 1.2 ቢሊዮን ብር ሰብስቦ አንድም መኪና አላስመጣም የሚለው ነው ብለዋል፡፡ ሌላው ደግሞ በራሱ በድርጅቱ የተመዘገበ የመኪና መገጣጠሚያ ፈቃድ የለውም የሚል እንደነበር ጠቁመዋል፡፡

"እውነቱ ግን ኦክሎክ ሞተርስ በመቀሌና በአዲስ አበባ በስሙ የተመዘገበ የመኪና መገጣጠሚያ ያለው ሲሆን፤ ከመኪና ፈላጊዎች የማህበራት አባላት የተሰበሰበው ገንዘብ 1.2 ቢሊዮን ብር ሳይሆን 41 ሚሊየን ብር ነው፡፡" ብለዋል፤ ሥራ አስኪያጁ፡፡

ኦክሎክ ከአባላቱ ገንዘብ ሰብስቦ ምንም መኪና አላመጣም የሚለውም ትክክል አይደለም ያሉት አቶ ታመነ ካሣሁን፤ የማህበሩ አባላት እስካሁን 800 ተሽከርካሪዎችን በካሽና በብድር ወስደዋል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

የሽማግሌዎቹ ቡድንም እኒህን የተሳሳቱ መረጃዎች በራሳቸው መንገድ አጣርተው፣ እውነታው ላይ መድረሳቸውን በራሳቸው አንደበት ያረጋገጡ ሲሆን፤ እርቅ ላይ የተደረሰውም ከዚህ ሁሉ ሂደት በኋላ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በሁለቱ ወገኖች መካከል የተፈጠረው ልዩነት በእርቅ መፈታቱን ያደነቁ የተለያዩ ማህበራት ተወካዮች፤ ሌሎችም በክስ ሂደት ላይ ያሉ ማህበራት ችግራቸውን በእርቅ የሚፈቱበት ሁኔታ ይመቻች ዘንድ ሃሳብ ሰንዝረዋል፡፡

ከኦክሎክ ሞተርስ ጋር የእርቅ ስምምነት ላይ መድረሳቸው የተገለጸው ከ60 ማህበራት ውስጥ 16 ያህሉ እንደሆኑ ለማወቅ ተችሏል፡፡

ከ20 ዓመት በፊት የተመሰረተውና በተለያዩ ዘርፎች ላይ የተሰማራው ኦክሎክ ሞተርስ፤ በትግራይ መቀሌ ከተማና በአዲስ አበባ ቃሊቲ አካባቢ ባስገነባቸው የተሽከርካሪ መገጣጠሚያ ፋብሪካዎቹ ከ16 በላይ የተለያዩ ሞዴል ተገጣጣሚ ተሽከርካሪዎችን ከውጭ በማስመጣት እየገጣጠመ ለደንበኞቹ በማቅረብ ላይ ይገኛል፡፡

መቅረዝ ሥነኪን ወርሀዊ የኪነጥበብ ዝግጅት የፊታችን ሐሙስ መጋቢት 4 ቀን 2017 ዓ.ም ከምሽቱ 11:00 ጀምሮ በብሔራዊ ቤተመዛግብትና ቤተመጻሕፍት አገልግሎት (ወመዘክር )አዳራሽ ውስጥ ይካሄዳል።

የእኛና የሌላኛዎቹ አለም ፍጡራን ነገር
…አጠቃላይ ቁመናው በወፍራም ብርሃንና ጨረር ተቀርፆ ይታየኛል እንጂ ዝርዝር መልኩን ማየት አልችልም። ደንግጫለሁ። የእግዚአብሔር ይሁን የሞት መልአክ ባላውቅም ከፊቱ በግንባሬ ወደቅሁ።
“ምን ሆንህ?” የሚል ንግግር ሰማሁ። የድምፁ አይነት ከሰው ልጅ ድምፅ ቃና ይለያል፣ ለጆሮ የሚከነክንና የሚሰቀጥጥ ቃና ነው። ከሆነ የዱር ወፍ፣ ከቆቅ ምናምን ጉሮሮ የሚወጣ ድምፅ ይመስላል፣ የቆቅ ያልሁት ከማውቀው ድምፅ ጋር ላቀራርበው ብዬ እንጂ በትክክል እንደ ቆቅም አይደለም፤ እና ትኩር ብዬ ስሰማው ድምፁ የሚያስፈራ ነገር አለው። ቋንቋው ግን ግልፅ የሆነ አማርኛ ነበር።
“የእግዚአብሔር መልአክ ሆይ በፊትህ እሰግዳለሁ” አልሁት እንደተደፋሁ ፊቴን ብቻ ቀና አድርጌ።
ሳቀ– በጣም አጭር፣ ቀድሞ የሚያቆም ሳቅ የሚመስል ነገር።
“የእግዚአብሔር መልአክ አይደለሁም” አለ።
“ምንድነህ”
“መጀመሪያ ተነስ። ተረጋጋ”
ተነስቼ ቆምሁ።
“ከሌላ ዓለም የመጣሁ ወንድምህ ነኝ” አለኝ።
“ሌላ ዓለም? …ከየት? እ… ምን ወንድም አለኝ…”
“ምን ወንድም አለኝ? ብታውቅበት በሁለንታው ውስጥ ያለው ሁሉ ወንድምህና እህትህ ነው። እኔ የፈጣሪያችሁ መንፈስ በጊዜና ቦታ አራርቆን የቆዬ ወንድምህ ነኝ”
“አልገባኝም እባክህ…”
“እሺ በሚገባህ ሰዋዊና ምድራዊ ዕሳቤ ልንገርህ፡ ከሌላ ፕላኔት ነው የመጣሁት”
“ሌላ ፕላኔት? ከየት?”
ሲነገር የነበረው ሁሉ እውነት ነው ማለት ነው?
“ዝርዝሩን ቆይ ቁጭ ብለን ትረዳለህ፣ አሁን ልረዳህ ነው ያገኘሁህ”
“ሰው ሳትሆን ምን ትረዳኛለህ? መንገዴን ባታሰናክለኝ እንደረዳኸኝ እቆጥረዋለሁ”
“እውነት እውነቱን ብቻ ንገረኝ፣ ወዴት ነው የምትጓዘው”
“እየሸሸሁ ነው”
“ከምን”
“ከሞት”
“ሞት ምንድነው”
“ሞት አላውቅም እያልኸኝ ነው? እያሾፍህ መሆን አለበት”
“አላውቅም ምንድነው”
“እንዴት ፍጡር ሆነህ ሞትን አታውቅም?”
“ትንሽ የተፈጥሮና የስልጣኔ ልዩነት አለን። ለዚያ ይሆናል ያላወቅሁት። እና ሞት ምንድነው”
***
“ሞት፡ ማንኛውም ባረን ለመጀመሪያም ለሁለተኛም ለሦስተኛም ጊዜ ስትነግረው የሰውን ልጅ ሞትና አሟሟት አምኖ ለመቀበል ይከብደዋል። በፈጣሪው አምሳል የተሠራ ፍጡር በእንቅፋት ይሞታል ብትለው ሊገባው አይችልም። የሞታችሁ ነገር እኔን እንኳን ለብዙ ዘመን ምድርን ያጠናሁትን ባረን ሁልጊዜ እንዳስገረመኝ ነው። ከሞታችሁ የበለጠ ደግሞ አሟሟታችሁ ያስገርመኛል። የምትሞቱበትን ጊዜ አታውቁም። አለማውቃችሁ ጥሩ፣ ግን ስትጓዝ እንደነበር በሆነ ምክንያት ልትሞት ትችላለህ። በበሽታ ልትሞት ትችላለህ። መኪኖቻችሁ ተጋጭተው ልትሞት ትችላለህ። እሳት ሊበላህ፣ ውሃ ሊወስድህ ይችላል። ከሕይወት ወደ ሞት ሽግግራችሁ ድንገተኛ ነው። እና አትመለሱም ደግሞ፣ ወይስ ትመለሳላችሁ? እሱን ፈጣሪያችሁ ነው የሚያውቀው። ኃያልና ደግ ፈጣሪ ነው ያላችሁ፣ ግን አበላሽቶ ነው የሠራችሁ”
***
“ሰማያዊው ጦርነት ባይቀድመን፣ ጉዞህን ቀጥለህ ለሁለተኛ ጊዜ ስንገናኝ ራስህን የተሻለ መንፈሳዊና አካላዊ ሁኔታ ላይ ታገኘዋለህ”
“ጦርነቱ መቼ ተጠናቆ እየሱስ ለመጀመሪያው ትንሳኤ ወደ ምድር የሚመለስ ይመስልሃል?”
“ምን ሊያደርግ ይመለሳል? ደግሞስ እየሱስ ብቻ ነው የሚመጣው? ቡድሃስ? ሞሀመድስ? ሙሴስ? ሌሎችስ አይመጡም? ደግሞስ ማን ያውቃል። ስለዚያች ቀን ከእግዚአብሔር በቀር መላእክትም ቢሆኑ፣ እየሱስም ቢሆን፣ ማንም ቢሆን የሚያውቅ የለም ይል አይደለም እንዴ መጽሐፋችሁ? ታዲያ ራሱ እየሱስ እንኳን የማያውቀውን ነገር እኔ ባረኑ እንዴት አውቃለሁ ብለህ ነው”
ባረኑ ሳቀና ቀጠለ፦
“ዛሬም፣ ነገም፣ ከነገ ወዲያም ሊሆን ይችላል፣ ወይም መቼምም ላይሆን ይችላል፣ እርግጠኛ ሆኜ የምነግርህ መጠበቅ አስፈላጊ እንዳልሆነ ነው። በመጠበቅ የሚመጣ ጊዜ የለም፣ ሁሉም ጊዜ ተሰጥቶ ያበቃ ነው”
***
የጊዜ ነገር
…በዙሪያዬ ማንም ምንም አልነበረም። በፀሀይና በሙቀት እየተቃጠልሁ በዚህ የቀትር ውቅያኖስ ባረጋው በረሃ መሀል ሳቋርጥ አንዳች ግዙፍ ነገር ከፊቴ ገጠመኝ። ቆምሁ።
“ምንድነህ ማነህ?” አልሁት። ፍርሀት የሚባል ነገር ከውስጤ ጠፍቷል።
“ጊዜ ነኝ” አለኝ።
“ጊዜ?”
“አዎ። የነበርሁ ያለሁና የተሰጠሁ”
“ኧረ ባክህ፣ ቀልደኛ። እሺ አቶ ጊዜ፣ ‘አቶ’ ልበልህ ወይስ ሌላ ማዕረግ አለህ?”
“የሁሉም ማዕረግ ባለቤት እኔ ነኝ፣ ሁሉም ከእኔ እየተዋሰ ነው የሚወስድ”
“ጊዜ እንዴት በአካለ ገጽ ሊገለጥ ይችላል?”
“ሁሉም ባለ አካለ ገፅ እኔ ውስጥ ነው ያለው፣ አንተ አሁን እኔ ውስጥ ነው ያለኸው”
“እዚህና እዚያ ለየብቻ ቆመን እንዴት እኔ ውስጥ ነው ያለኸው ትለኛለህ”
“መስሎህ ነው”
“እውን ጊዜ የምትባለው አንተ ነህ?”
“ጊዜ ነኝ፤ ስንቱን ከወደቀበት አመድ ላይ የማስነሳ፣ ለበደለኛ አበሳውን ለፃድቅ ዋጋውን የማልነሳ፣ ስንቱን ገናና እንዳልነበረ የምደመስስ። የሁሉም ነገር መጀመሪያና መጨረሻ እኔ ጊዜ ነኝ”
***
የፍቅር ነገር
…ምድራችን ለዘላለም ፀሐይን ስትዞር ትኖራለች። የእኔም ልብ ከዚህ ወዲያ ከአንዲት ፀሐይ የመሰለች የሴት ልጅ ምህዋር መውጣት የምትችል አልመስልህ አለኝ። ልቤ አሁን ላይ ከሀገረ-ዘላለማዊት ምህዋሯ ተጎትታ ወጥታ የምትዞረው በሰማንያ ስምንቷ ዙሪያ ነው። በሀይለኛው የሰማንያ ስምንቷ የስበት ወጥመድ ተይዤያለሁ። ምድር በፀሐይ፣ ጨረቃ በምድር ስበት ተይዘው እንደቀሩት ሁሉ እኔም የሰማንያ ስምንቷ የፍቅር ግራቪቲ እስረኛ ሆኜ እንዳልቀር ሰግቼያለሁ።…ቢሮዋ ሄጄ ያየኋት እለት ሌሊቱን ሁሉ በእንቅልፍ ልቤ ሳስባት ነው ያደርሁት። ተኝቼም ነቅቼም የማልመው እሷን ነበር። …
***
የትናንሽ ማንነቶቻችን ነገር
…የሰው ልጅ ሲወለድ ንፁህ ነው፣ ሰው ብቻ ነው። እያደገ ሲሄድ በትናንሽ ማንነቶች ይቆሽሻል። መጀመሪያ በሃይማኖት ጣሳ ውስጥ ያስገቡታል፤ ከዚያ በጎሳ፣ በብሔረሰብና በሀገር ብሔርተኝነት ገመድ ይተበትቡታል፤ ከዚያ የታሪክ፣ የፖለቲካና የርዕዮተ-ዓለም ሸክም ይጭኑታል። አደግሁ፣ በሰልሁ ሲል እውነቱን በእነዚህ ትናንሽ ማንነቶች ውስጥ አጥሮ ይገነባል። በዚህ አጥር ውስጥ እንደኳተነ በመጨረሻም እውነተኛ ማንነቱን ሳያውቅ ያልፋል። …
***
የኢትዮጵያ ነገር
ሳንዶብ ቆይቶ ኢትዮጵያ መሄድ ከንፁህ ቤት ወጥቶ ጭቃ ውስጥ እንደመግባት ነው። ሀገሬን ስለማልወድ አይደለም እንደዚያ የምለው፣ ጨለምተኛ ሆኜም አይደለም። እውነታው እንደዚያ ስለሆነ ነው። ኢትዮጵያን በተቀባባ እውነት እየለደሱ እያቀረቡ ሀገር ወዳድ መስሎ መታየት አያዋጣም፣ ለማንም አይጠቅምም። የሚጠቅመው እውነታውን ተረድቶ ሀገሪቱን ለማሰልጠን ቆርጦ መነሳት ነው። ኢትዮጵያውን ያለፈ ታሪካቸውን ኩራት እያንቀራጩ (እና በእሱም እየተናጩ) ፈዘው የቀሩ ህዝቦች ሆነዋል። ኢትዮጵያውያን በታሪክና ትርክት፣ በጎሳ ፖለቲካና በአሮጌ ልማድ ውስጥ ተሰንቅረው ቀርተዋል። ሁለ ዓለማቸውን ስንቅሩ ውስጥ ሠርተዋል። ራዕያቸው ከስንቅሩ ወጥቶ ወደ ሁለንታው ዓለም መቀላቀል አይደለም፤ ይብዛም ይነስ ራዕያቸው አንዱን ወደ ቀዳዳው ገፍቶ ስንቅሩ ውስጥ የተሻለ ቦታ መያዝ ነው። …
***
የጦርነትና የህዋ ስልጣኔ ነገር
…አዎ፣ የሰው ልጅ ለህዋ ስልጣኔ የሚሆን ገንዘብ የለውም። ምክንያቱም፣ ምድር ላይ ያለውን ችግር አልፈታም። ቢሊዮኖች ዶላር በሙስና ይዘረፋል፣ ቢሊዮኖች ዶላር በባለሀብቶች ከንቱ ቅንጦት ይወድማል፣ ቢሊዮኖች ዶላር እየመደበ አንዱ ሀገር ሌላውን ይሰልላል፣ ትሪሊየኖች ዶላር ለጦር መሣሪያ መግዣና ለጦርነት ማድረጊያ ይወጣል፣ ጦርነቱ ትሪሊየኖች ዶላር ያወድማል። ጦርነቱ ያወደመውን ለመጠገን እንደገና ትሪሊየኖች ዶላር ይወጣል። ባለ መከራው እንባው ታብሶ፣ የወደመው ተጠግኖ ሳያበቃ እንደገና ትሪሊየኖች ዶላር የሚያጠፋ ሌላ ጦርነት ይፈነዳል። ምድር ያለቺው በዚህ የጥፋት አዙሪት ውስጥ ነው። ታዲያ እንዴት የሰው ልጅ ለህዋ የሚሆን ገንዘብ ሊኖረው ይችላል? እንዴትስ በቢሊየን የሚቆጠር ህዝብ እየተራበ፣ እየተሰደደና በበሽታ እያለቀ ለህዋ ምርምር ገንዘብ የማውጣት ሞራል ሊኖረው ይገባል? የህዋ ስልጣኔ ለሰው ልጅ ቅንጦት ሳይሆን ህልውና ነው። ይህ የሚሳካው ግን የሰው ልጅ ስር የሰደዱ ችግሮቹን ፈቶና ትናንሽ ማንነቶቹን አውልቆ ጥሎ ሰዋዊና ፕላኔታዊ አንድነት መገንባት ከቻለ ብቻ ነው።
***
የፕላኔታችን መልካም እጣ
የብዙ ሰዎች ሕልም መጓዝና ጥበብን ማድነቅ ይሆናል። በአንድ ፕላኔታዊ ፌደሬሽን በታቀፈች፣ ሰላም ፍትሕና ስልጣኔ በሰፈነባት ዓለም ላይ ስፖርት፣ ኪነጥበብና ቱሪዝም የምድራችን ቀዳሚ ታላላቅ ኢንዱስትሪዎች ይሆናሉ።

መጻሕፍት በዘመናት ሁሉ የሰውን ልጅ ህይወት ለመለወጥ ከፍተኛ ድርሻ ይኖራቸዋል፡፡ ቤንጃሚን ፍራንክሊን፣ አብርሃም ሊንከን፣ አይዛክ ኒውተንና ሄለን ኬለርን ብቻ እንኳን ብንወስድና በህይወታቸው መፅሐፍ ያስከተለውን ለውጥት ብንመረምር ብዙ እንረዳለን፡፡
ቤንጂሚን ፍራንክሊን በ17 ዓመቱ በፈላዴልፌያ ዋና ዋና መንገዶች የሚንከላወስ ቤሳቤስቲን የሌለው ምስኪን ወጣት ነበር፡፡ ወደፊት ሚስቱ የምትሆነውን ዴቦራን ያገኘው በዚህ ሁኔታ ነበር፡፡ በመጨረሻ ሳንቲሙ የገዛውን ዳቦ እየበላ በደጇ ያልፍ ነበር፡፡ የኮሌጅ ትምህርቱን ከመከታተል ይልቅ የምርጥ ምርጥ ደራሲያን ስራ ውጤት የሆኑ መፃህፍትን ማንበብና አእምሮውን ማበልፀግን መርጧል፡፡ ለቤንጃሚን ፍራንክሊን መፃሕፍት የማይለዩት ባልንጀሮቹ ነበሩ፡፡ መፅሐፍ ተውሶ ሌሊት ሲያነብ አድሮ በነጋታው ይመልስ ነበር፡፡ መጻሕፍቱ እጅግ አመርቂና መሰረት የያዘ የዓለም አቀፍ ፖለቲካ እውቀትን ያጎናፀፉት ሲሆን፤ በዚህም በዘመኑ የአሜሪካ ዲፕሎማት ሆኖ ነበር፡፡ ታሪክ ፀሀፊው ጊበን አንድ ጊዜ እንዲህ ብሎ ነበር፡- “የእኔን የጠዋት ንባብና ማንም የማይሽረውን የማንበብ ፍቅር ህንድ ባላት ሀብት ሁሉ እንኳን የምለውጠው አይደለም፡፡” ቻርለስ ዲከንስ ደግሞ “ለጥሩ መፃህፍት ያለኝ ፍቅር የተለያዩ ነገሮች እንዳያማልሉኝ እንደመከላከያ የቆመልኝ ጋሻ ጃግሬዬ ነው፡፡” ሲል በይፋ ገልጽዋል፡፡
ጣሊያናዊው ሲሴሮ ያለውን ንብረት ሁሉ ሸጦ መፃሕፍት ለመግዛትና ከመፃህፍት መካከል ለመኖርና ለመሞት የፈቀደ ሰው ነበር፡፡ ሲሴሮ የመጻሕፍትን ባህሪ ተንተርሶ እንደገለፀው፤ “ከመኖሪያ ቤቴ በተጨማሪ መጻሕፍት ቤት ባቋቁም ለቤቱ ነብስ ሰጠሁት እንደ ማለት ነው” ብሏል፡፡
አንድ ፀሀፊ ደግሞ እንዲህ ብሎ ነበር፤ “ማንም እኔን በቤተ-መንግሥት ውስጥ የሚኖር በአትክልትና በጽጌያት የተከበበ፣ በመልካም ግብር ድግስ፣ ጠጅ የተጣለበት፣ ሙክትና ፍሪዳው የሚታረድበት፣ በዘበኞች የተጠበቀ የታላቆች ታላቅ የሆነ፣ እስከዛሬ በዓለም ያልታየ ንጉስ ሊያረገኝ የሚችል ሰው ቢኖርና መፅሐፍ ግን አታነብም የሚለኝ ከሆነ፣ ንጉስነቱ በአፍንጫዬ ይውጣ እለዋለሁ፤ ከቶውንም የመጻሕፍት ፍቅር የሌለው ንጉስ ከምሆን፣ ጉሮኖ ውስጥ ደሃ ሆኜ ከብዙ መጻሕፍት ጋር ብቀመጥ እመርጣለሁ፡፡”
አይዛክ ኒውተን በወጣትነት እድሜው በባቡር ጣቢያ አካባቢ ጋዜጣ አዟሪ ነጋዴ ነበር፡፡ ባቡር እስከሚመጣ ድረስ በአካባቢው ከሚገኘው ቤተ መጻሕፍት አይጠፋም ነበር፡፡ ባቡሩ ሲመጣ ግን ጋዜጣውን ለመሸጥ ወደ ባቡር ጣቢያው ይመለስ ነበር፡፡
ሄለን ኬለር ዓይነ ስውር ነበረች፡፡ ሆኖም በነበራት መንፈሰ - ጠንካራነት በርትታ በመማርና ብዙ መፃሕፍትን በማንበብ የአሜሪካ የህግ መወሰኛው ምክር ቤት አባል ለመሆን የቻለች አስደናቂ ሴት ነበረች፡፡
በሀገራችን ያለው የንባብ ሁኔታ ምን ይመስላል?
በበለፀገው ዓለም እያንዳንዱ ቤተሰብ ሁለት በጣም አስፈላጊ የሆኑ ክፍሎች አሉት፡፡ አንደኛው ለአካል አስፈላጊ ምግቦችን መመገቢያ ሲሆን፤ ሌላኛው ደግሞ የአእምሮ ምግብ የሚገኝበት የንባብ ክፍል ነው፡፡ በነዚህ ሀገራት የአብዛኛው ቤተሰብ የንባብ ክፍል ስፋት ከመመገቢያ ክፍል ስፋት ይበልጣል፡፡ እርግጥ ነው ጣእም ከሰው ሰው ይለያል፡፡ እነዚህ አገሮች ለመፃሕፍት የሚያወጡት ወጪ ከግሮሰሪ ወጪያቸው የበለጠ መሆኑ ይታወቃል፡፡
በነዚህ አገራት የአንባቢው ቁጥር ባለፉት 50 ዓመታት ከፍተኛ እድገት ሲያሳይ፣ በያንዳንዱ ቤተሰብ ውስጥ መቶ መጻሕፍት ይገኛል፡፡ በኛስ አገር? የገጠሩን ህዝብ ለጊዜው እንተወውና፣ ዋና ዋና ከተሞችን እንኳን ብንወስድ፣ ልጆቻችን በየቤታችን መጻሕፍት ያገኛሉ?
በበለፀጉት አገራት በየ100 ሜትሮቹ ቤተ መጻሕፍት ወይም የመጻሕፍት መሸጫ መደብሮች ይገኛሉ፡፡ በኛም ሀገር ከግማሽ ሚሊዮን የሚበልጡ ኪዮስኮች አሉ - የተለያዩ ቁሳቁሶች የሚቸረቸርባቸው፡፡ በሀገሪቱ ባጠቃላይ የአሮጌ መጻሕፍት መሸጫ መደብሮች እንኳን ጨምረን አንድ መቶ እንኳን የሚሞሉ መጻሕፍት መደብሮች የሉም፡፡ በርግጥ ንግዱ በሀገራችን አትራፊ የሚያደርግ አይደለም፡፡ ለዚህም ይሆናል ሜጋ ከኩራዝ የተረከበውን የመርካቶውንና ከአራዳ ገበያ ፊት ለፊት የሚገኙትን የመጻሕፍት መደብሮች ወደ ኤሌክትሮኒክስ እቃዎች መቸርቸሪያነት የለወጠው፡፡ (ልብ በሉ! ጽሁፉ በ1992 ዓ.ም የተጻፈ ነው) አስተያየቴ የሚስቀይማቸው ቢኖሩ በቅድሚያ ይቅርታ እጠይቃለሁ፡፡ ለመሆኑ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥንም ሆነ ሬዲዮ 10 እንኳን የሚሞሉ መጻሕፍት ሲተዋወቁ አይተናል? ወይስ ሰምተናል?
ባሉትም የመጻህፍት መደብሮች በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ አዳዲስና አሮጌ መጻሕፍት ተደርድረው ቢውሉም፣ ሊጎበኙአቸው ወደ መደብሮቹ የሚሄዱት በጣት የሚቆጠሩ ናቸው፡፡ ከነዚህም ውስጥ የሚፈልጉትን የመጻሕፍት ዓይነት በትክክል የሚያውቁትን ቁጥራቸውን ባልናገር ወይም ባልገምት ይሻላል፡፡ አሳፋሪ ነውና፡፡ ለመሆኑ ስንቶቻችን በዓመት 5 መጻሕፍት እንገዛለን? ቁጥሩን አበዛሁት እንዴ? (ይቅርታ ትልቅ ይቅርታ!!)
ተዳፈርክ ባልባል በአብዛኛው የሃበሻ ቤት ውስጥ መጻሕፍት ቢሰበሰቡም እንኳን ቤት ማሳመሪያ ተደርገው ነው የሚታዩት፡፡ ያሳዝናል! መጻሕፍት ሊያገለግሉን እንጂ ለትርኢት የሚቀመጡ አልነበሩም፡፡ እውነተኛ አንባቢዎች ወይም የሚፍጨረጨሩ የሚተጉ /ለማንበብ/ የሉም ማለቴ እንዳልሆነ ተረዱኝ፡፡ የአንባቢው ቁጥር በሚያሳዝን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ለማሳየትና ሁኔታውን ለመለወጥ ከያንዳንዳችን ብዙ እንደሚጠበቅ ለማሳየት ካለኝ ቅን ፍላጎት ነው፡፡ ዶ/ር ሳሙኤል ጆንሰን አንድ ጊዜ፤ “የማያነቡ ሰዎች የሚያስቡት ነገር አይኖራቸውም፤ የሚናገሩትም እጅግ ጥቂት ነው፡፡” ብለው ነበር፡፡
በሀገራችን ብዙ ተማሪዎች “ትምህርት ጨርስኩ” የሚል አባባል ሊሰነዝሩ ይደመጣሉ፡፡ እኔ ይህን አባባል የምደግፍ አይደለሁም፡፡ የአንድ እንግሊዛዊ ምሩቅ ተማሪና መምህር ምልልስን እንመልከት፡፡ በዩኒቨርሲቲ የምርቃት በዓሉ ላይ በደስታ ተሞልቶ የመጣ አንድ ወጣት ተማሪ ለኮሌጁ ፕሬዚዳንት ትምህርቱን በድል ማጠናቀቁን ጮክ ብሎ ነገረው፡፡ ፕሬዚዳንቱም፤ “እኔ እንኳ ገና መጀመሬ ነው” ሲሉ መልስ ሰጡት፡፡ በሀገራችን አብዛኛዎቹ ወጣቶች ከአንድ ኮሌጅ ወይም ዩኒቨርሲቲ ከተመረቁ በኋላ መጻሕፍት በዓይናቸው ላለማየት የማሉ ይመስላል፡፡ የተሳሳትኩ አይመስለኝም፡፡ ለአባባሌም ይቅርታ አልጠይቅም፡፡
(አዲስ አድማስ፤ግንቦት 12 ቀን 1992 ዓ.ም)

“--እንዲህ ነው፣ አስተማሪ፡፡ አስተማሪ አዋላጅ ነው፡፡ እኛ ግን አኮፋዳ እንድንሆን የተደረግን ይመስለኛል፡፡ አስተማሪ ተማሪው የያዘውን እንዲወልድ
ያግዘዋል እንጂ እርሱ ሊያረግዝለት አይችልም፡፡ ተማሪው መክኖ እንዳይቀር (እውነተኛ ተፈጥሮውንና ማንነቱን እንዲጸንስ) ምክንያት ይሆነዋል፡፡--”


ፍልስፍና ከሚመረምራቸው ዋነኛ ጉዳዮቹ መካከል የሰው ልጅ መነሻ ከየት ነው? መድረሻውስ (መጨረሻው (መጨረሻ ካለው)) ምንድነው? ዕጣ-ፋንታው ተወስኗል ወይስ አልተወሰነም? (ነፃ ፈቃድ አለው ወይስ የለውም?) ሰው ‘በልቡ እንዳሰበው’ ይኖራል ወይስ ሕይወቱን የሚዘውርለት ሌላ ‘አካል’ አለ? የልቡ ሃሳብስ ቢሆን የራሱ ነው ወይስ የሌላ? የሚሉት ጥያቄዎች የታላላቆቹ ፈላስፎች ጠረጴዛ ላይ ሲነሱና ሲወድቁ የኖሩ የመሟገቻ ሃሳቦች ነበሩ። አርስቶትል (Nicomachean ethics, book III)፣ ቅዱስ ኦገስቲን (City of God, book V, and On free choice of the will)፣ ቅዱስ ቶማስ አኩዊናስ (Summa theologica First Part Question 19, anf Question 83)፣ ሙሴ ማይሞኒደስ (the guide for the perplexed)፣ ስፒኖዛ (the ethics)፣ ሳርትር (being and nothingness)፣ ኒቼ (beyond good and evil)… ሌሎችም በርካቶች በእጃቸው ላይ የሚገኙትን ጠጠሮች በተለይ በነጻ ፈቃድ ጉዳይ ላይ ወርውረው አልፈዋል። ጉዳዩ ስለ ሰው ልጅ ነውና በአማኝም በኢ-አማኝም ዓይን ተመርምሯል። ከፈላስፋ ጀምሮ ከመነኩሴ እስከ ሳይንቲስት የምለው አለኝ ብለው በደረሱበት ልክ ሃሳባቸውን ገልጸዋል። የሰው ልጅ ነፃ ፈቃድ አለው፤ ዕጣ-ፋንታው አልተወሰነም የሚሉ፣ ዕጣ-ፋንታው ተወስኗል የሚሉ፣ ሁለቱ ሃሳቦች የሚታረቁ ናቸው የሚሉ እና እግዚአብሔር ነገሮች ከመሆናቸው በፊት ማወቁ ከነፃ ፈቃድ ጋር አይጋጭም የሚሉ ወዘተ አስተሳሰቦች ተነስተዋል። ያም ሆኖ የሰው ልጅ ምድር ላይ እስካለ ድረስ ጉዳዩ በየጊዜው እየተነሳ የሚመረመር እንጅ መዝገቡ ተዘግቶ ወደ መዝገብ ቤት የሚመለስ አይደለም። በሀገራችንም ቢሆን የተለያዩ ሰዎች ነገሩ አሳስቧቸው አመለካከታቸውን በየስራዎቻቸው ላይ በቀጥታም በተዘዋዋሪም አስቀምጠው አልፈዋል።
ድምጻዊ ይርጋ ዱባለ በአንድ ሙዚቃው ላይ፤
የሚሆን ይሆናል የማይሆን አይሆንም
ለቁጥቋጦ ያለው መቼም ዛፍ አይሆንም ይላል።
በዕውቀቱ ስዩምም ከይርጋ ጋር በሃሳብ እንደሚስማማ የሚያሳዩ ግጥሞች አሉት። ለምሳሌ ያህል ብቻ በስብስብ ግጥሞች መድበሉ ውስጥ የምትገኝ አንዲት ቁመተ-ዶሮ (አጭሬ ግጥም ቁመተ-ዶሮ እንዲሉ ሊቁ ኪዳነወልድ ክፍሌ) ግጥሙን እንጥቀስ።
እግዜርና ዳዊት በአንድ ተቧደኑ
ብቻውን ታጠቀ ጎልያድ ምስኪኑ
አንዳንዱ ተገዶ ለሽንፈት ሲፈጠር
በጥቅሻ ይወድቃል እንኳንስ በጠጠር። ይላል።
ይህን ሃሳብ የሚያጠናክር አስተሳሰብ በኤፍሬም ስዩም ስራ ውስጥም እናገኛለን።
…በተጻፈ ተውኔት
ባለቀ ዝግጅት
አሜን ማለት ከላይ መብረር
ለምን ማለት ክንፍን መስበር…
እያለ የሰው ልጅ ዕጣ ፋንታ ፅዋ ተርታ፣ የተጻፈውን ተውኔት በስክሪፕቱ መሰረት መተወን ብቻ እንደሆነ አስረግጦ ይከራከራል። በርከት ያለው ሕዝባችንም ቢሆን (ጥናት የሚጠይቅ መሆኑ እንዳለ ሆኖ) አስተሳሰቡ የሰው ልጅ ዕድል አስቀድሞ ተወስኗል ወደ ሚለው ያደላል። ከፈጣሪው ጋር የሚጣላ ስለሚመስለው ነፃ ፈቃድ አለኝ እያለ ይሽኮረመማል እንጅ አኗኗሩ፣ ስነ-ቃሉም፣ ስነ-ግጥሙም ሲመረመር ግን ‘ለቁጥቋጦ ያለው መቼም ዛፍ አይሆንም’ የሚለውን አስተሳሰብ የሚያንጸባርቅ ነው።
ዕድሌ ነው እንጅ ከሰው ያሳነሰኝ
ብርቱካን ሲታደል ሎሚ የደረሰኝ -- እያለ ከእሱ ቁጥጥርና ፈቃድ ውጭ የሆነ ኃይል ሕይወቱ ላይ እንደሚወስን ይመሰክራል። ‘ይታደሉታል እንጅ አይታገሉትም’ ብሎ አጉል መፈራገጥ ትርፉ መላላጥ እንደሆነ ይናገራል። ‘የአርባ ቀን ዕድሌ ነው’ የሚለው አገላለጽም ቢሆን በሀገራችን የተለመደ መሆኑ እርግጥ ነው። ከእነዚህ የ’ተወስኗል’ አስተሳሰቦች በተቃራኒ የምናገኛቸው አሳቢዎች በአንጻሩ ጥቂት የሚባሉ ናቸው። ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም ለደህነታችን ዋነኛው መንስኤ ይህ አስተሳሰባችን እንደሆነና ሊቀየርም እንደሚገባው ‘ኢትዮጵያዊነት ከየት ወዴት?’ በሚለው መጽሐፋቸው ላይ በስፋት ያብራራሉ። ይስማዕከ ወርቁ ደግሞ በአንድ ግጥሙ ላይ ጉዳዩን በጨረፍታ ነክቶት ያልፋል።
የተኛ በቆሎ ጎርፍ የደፈጠጠው
ተኝቶም ያፈራል ትል እያላመጠው
ድንጋዩን ሳይጫን አፈሩን ሳይለብሰው
መፈርጠጡስ ይቅር መዳህ ያቅተዋል ሰው?
ሰው አፈር እስካልለበሰ፡ ክንዱን እስካልተንተራሰ ድረስ ሕይወቱን በትግሉ የመለወጥ ኃላፊነት እጁ ላይ እንደሆነና ይህን ለማድረግም ነጻ ፈቃድ እንዳለው በተዘዋዋሪም ቢሆን ይጠቁማል።
የነጻ ፈቃድ ጉዳይ እንግዲህ ማንነታችንን ስናሰላስል አስቀድመው ከሚመጡልን ግዙፍ ጥያቄዎች አንዱ ሲሆን፤ ከዚህ ግዝፈት በታች የሆኑ ሌሎች ንዑስ ጥያቄዎች ደግሞ አሉ። (ንዑስ የተባሉት ከዕጣ-ፋንታ ጥያቄ ግዝፈት አንፃር ሲታዩ እንጅ ራሳቸውን አስችለን ነጥለን ስንመለከታቸው ግን በየራሳቸው እጅግ ግዙፍና ውስብስብ ናቸው) ከእነዚህ ‘ንዑስ’ ጥያቄዎች አንፃር የነጻ ፈቃድ መኖር አለመኖር ላይ መከራከር ቅብጠት ነው። ለጊዜው ዕጣ-ፋንታችን ተወስኗል የሚለውን ጥለን፤ ነጻ ፈቃድ አለን የሚለውን አንጠልጥለን ብንቀጥል እንኳ አሁን ‘እኔ’ የምንለው ማንነታችን በእርግጥም በነጻ ፈቃዳችን የመረጥነው እውነተኛው ‘እኔነት’ ነው ወይስ በሌሎች ሰዎችና በማኅበረሰባችን ተጽዕኖ የተፈጠረ ሀሰተኛ ማንነት ነው? የሚለው ከእያንዳንዳችን ፊት የቆመ ጥያቄ ነው። መነሻው የትም ይሁን ሕይወት መንገድ ነው። ከእናታችን ማህፀን ከወጣንባት ቅፅበት ጀምሮ (ምናልባት ከዚያም በፊት ጀምሮ) በዚህ መንገድ ላይ ተገኝተናል። መንገዱ በአሳባሪዎች የተሞላ እንደመሆኑ መጠን (በመረጥነው) አሳባሪ ስንጓዝ፣ አረማመዳችን ራሳችንን ይመስላል ወይ? መስለን የምንታየውና በትክክልም የሆንነው ማንነታችን አንድ አይነት ናቸው ወይስ እንደ ልብሶቻችን የክት እና የአዘቦት ‘ማንነት’ አለን? ፈጣሪ (ወይም ተፈጥሮ) ዕጣ-ፋንታችንን ወስኗል ወይም አልወሰነም ከማለታችን በፊት፣ የእኛ ዕጣ-ፋንታና ነጻ ፈቃድ ማኅበረሰቡ በሰራው ቅርጽ (ሞልድ) ውስጥ ገብቶ አልተጨፈለቀም ወይ? ከላይ ከተብራራው የነጻ ፈቃድ ጉዳይ ይልቅ ይህኛው ጥያቄ ለሰው ልጅ የበለጠ ተግባራዊ ጠቀሜታ ያለው ይመስላል። ወደ ሰማይ ከማንጋጠጣችን በፊት መጀመሪያ የጎንዮሹ ምን ይመስላል የሚለውን መመርመር አስፈላጊ ነው። ፈጣሪ ነጻ ፈቃድ ሰጥቶን ከሆነ እኛስ በተሰጠን ነጻ ፈቃድ ልክ በነፃ ምርጫችን እየኖርን ነው ወይ? ማኅበረሰባዊ ድጋፍ (Social approval) ለማግኘት ስንል የማንመርጠውን አልመረጥንም? የማንፈልገውን አልሆንም? የምንጠላውን የምንወደው አልመሰልንም? ራሳችንን እየኖርን ነው ወይስ የሆነ ሰውን እየተወንን? የሕይወታችን ደራሲዎች ነን ወይስ ማኅበረሰብ የጻፈልንን የማንነት መነባንብ አነብናቢዎች? ከዋነኛው የዕጣ-ፋንታ ክርክር በፊት ይህን ጥያቄ ማንሳት የሚያስፈልገው ሞኝ ላለመሆን ነው።
ፈጣሪ በፈቀድነው መንገድ እንድንኖር ቢፈቅድልንም፣ ፈቃዳችንን ካልኖርነው፣ እኛ ላይ ያለው ነጻ ፈቃድ ‘መቃብር ላይ እንደተቀመጠ ጣፋጭ ምግብ’ መሆኑ እርግጥ ነው። መኖሩም አለመኖሩም ትርጉም አይሰጥም። ወደ ውሃው ወይም ወደ እሳቱ እጃችንን የመስደድ ምርጫ ቢሰጠንም እንኳ እጃችንን የምንሰደው ወደፈለግነው ሳይሆን ማህበረሰብ (ወይ ሰዎች) እንድንሰድበት ወደሚፈልጉት ከሆነ፣ የተሰጠንን ነፃ ፈቃድ አክስረናል። በዚህም የተነሳ ሕይወትን አክስረናል፤ አርክሰናልም። ይህ እንግዲህ እንደ አለመታደል ሆኖ የአብዛኞቻችን የዕለት ተዕለት የአኗኗር ዘዬ ነው። ከእውነተኛው ማንነታችን ጋር ተካክደን ለወል ፍላጎት እጅ ሰጥተናል። የግል እውነታችንን ለመንጋው ፍላጎት ባርያ አድርገናታል። ለጥፊ የዘረጋነውን እጅ (በይሉኝታ ወይም በማስመሰል የተነሳ) ሃሳባችንን ቀይረን አጨብጭበንበታል። ሰዎች ሲወዱት አይተን፡ የማንፈልገውን ተምረናል። የሚያስመልሰንን በልተናል። ጥሩ ሰው መሆናችንን ለማረጋገጥ የማኅበረሰቡን ‘የጥሩ ሰውነት መስፈርት’ ሸምድደን ተውነናል። ኤርቪንግ ጎፍማን የተባለ የማኅበረሰብ አጥኚ እ.ኤ.አ በ1959 the presentation of self in everyday life በሚል ርዕስ ባሳተመው ጥናቱ፤ የእያንዳንዳችን የየዕለት ግንኙነት (daily interaction) ትወና መሆኑን ያስረግጣል። ግላዊ ማንነታችንን ትተን ማኅበረሰቡ እንድንሆን የሚጠብቅብንን ማንነት ስናሳድድና እሱኑ ስንተውን ከእውነተኛው እኛነታችን ጋር እንተላለፋለን። አስቀድሞ ከተሰራው ቅርጽ ጋር እንድንገጥም ሲባል ራሳችንን በራሳችን ከርክመን ከርክመን ሌላ ሆነን እናርፈዋለን።
ለመመሳሰል ስንል ልዩነታችንን በህዝብ ቀለም እንደልዛለን። ባዶ እጁን የቆመ ማኅበረሰብ መሐል ስለተገኘን ብቻ አንዳች ነገር ይዘን መወለዳችን ኃጢአት መስሎ ይታየንና፣ የያዝነውን ደፍተን ከባዶው መሐል ባዷችንን ገብተን እኩል እንሆናለን። ከዚያ በኋላ የሚኖረን እድል (ያውም ከነቃን) “እንዲህ ነበርኩ እንዴ?” ብለን መጠየቅ ነው። ፈጣሪም ገና ሲያየን በሚላን ኩንዴራ አገላለጽ፤ “እሱ ነው፤ ግን እሱን አይመስልም” ብሎን ያልፋል። ሕይወታችን ይህ ከሆነ ነጻ ፈቃድ ኖረ አልኖረ ፋይዳው ምንድነው?


ከአድማስ ትውስታ ፤ 1992

አሸናፊዎች በአሜሪካ በሚካሄደው ዓለማቀፍ የሮቦቲክስ ውድድር ላይ ይሳተፋሉ


3ኛው ዙር የአፍሪካን ሮቦቲክስ ሻምፒየንሺፕ ውድድር ከመጋቢት 4 እስከ 6 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሳይንስ ሙዚየም እንደሚካሄድ ኢትዮ ሮቦቲክስ አስታወቀ፡፡ ከፊታችን ሐሙስ ጀምሮ ለሦስት ተከታታይ ቀናት በሚካሄደው በዚህ ውድድር የመጀመሪያ ደረጃ፤ የሁለተኛ ደረጃ፣ የኮሌጅና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እንደሚወዳደሩ የተገለጸ ሲሆን፤ውድድሩ በዲዛይኒንግ፤ በኢንጅነሪንግና በአውቶነመስ ኮዲንግ ላይ እንደሚያተኩር ታውቋል፡፡
በውድድሩ አሸናፊ የሚሆኑ ተማሪዎች የዋንጫ ሽልማቶችን የሚያገኙ ሲሆን፤ በኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር የተፈረመ ሰርተፊኬትም ይበረከትላቸዋል ተብሏል፡፡ በዚህ ውድድር በአዲስ አበባ የሚኖሩ አፍሪካውያንም የሚካፈሉ ሲሆን፤ ለፍጻሜ የሚበቁ ተማሪዎች አገራቸውን ወክለው በአሜሪካ በሚካሄደው ዓለማቀፍ የሮቦቲክስ ውድድር ላይ እንደሚሳተፉ የኢትዮ ሮቦቲክስ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሰናይክረም መኮንን ገልጸዋል።
ላለፉት 15 ዓመታት የነገዎቹን ኢንጂነሮችና ፕሮግራመሮች የመፍጠር ራዕይ ሰንቆ ሲሰራ የቆየው ማዕከሉ፤ ኢትዮጵያውያን ታዳጊዎች በዓለማቀፍ የሮቦቲክስ ውድድሮች ላይ እንዲሳተፉና ዓለማቀፍ ልምድና ተሞክሮ እንዲቀምሱ በማድረግ ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል፡፡ ባለፈው ዓመት በቻይና ሻንጋይ በተካሄደው ኢንጆይ ኤአይ ዓለማቀፍ የሮቦቲክስ ውድድር ላይ 21 ኢትዮጵያውያን ታዳጊዎች ሀገራቸውን ወክለው የተወዳደሩ ሲሆን፤ በውድድሩ ከተሳተፉ 27 የዓለም አገራት 3ኛ ደረጃን ይዘው ማጠናቀቃቸው ይታወሳል፡፡
በተመሳሳይ፣ ዓምና በአሜሪካ በተካሄደ የዓለም ሮቦቲክስ ሻምፒዮን የተሳተፉ ታዳጊዎች አስደማሚ ውጤት ያስመዘገቡ ሲሆን፤ ይህን ተከትሎም የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር “ታዳጊዎቹ ኢትዮጵያን በዓለም መድረክ ማስጠራት ጀምረዋል” ሲል ዕውቅና ሰጥቷል፡፡
የኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ዕውቅናና አድናቆት በመስጠት ብቻ ግን አልተወሰነም፡፡ ኢትዮ ሮቦቲክስ የጀመረውን ታዳጊዎችን በቴክኖሎጂ የማሰልጠንና የማብቃት ሥራን አጠናክሮ እንዲቀጥል ሙሉ ድጋፍ እያደረገ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡
የኢትዮ ሮቦቲክስ መሥራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ሰናይክረም መኮንን እንደሚሉት፤ ማዕከላቸው ታዳጊዎችን ከማሰልጠንና በዓለማቀፍ ውድድሮች እንዲሳተፉ ዕድሎችን ከማመቻቸት የሚዘልቅ ራዕይን ሰንቋል፡፡ እንደ ቻይናና ሌሎች ያደጉ አገራት ሮቦቲክስ በመደበኛ የትምህርት ሥርዓት ውስጥ እንዲካተት ፍላጎት እንዳላቸው የተናገሩት ዋና ሥራ አስፈጻሚው፤ ለዚያም በትጋት እየሰራን ነው ብለዋል፡፡

 

Page 1 of 758