Administrator

Administrator

ድምጻዊ ቴዎድሮስ አሰፋ (ቴዲ ዮ) ከዞጃክ ወርልድ ዋይድ ጋር በመተባበር ያዘጋጀውን  “ይለያል” የተሰኘ ሦስተኛ አልበሙን በትላንትናው ዕለት ለገበያ ማቅረቡ ታውቋል፡፡ ሦስተኛ አልበሙ መውጣቱን አስመልክቶ ድምጻዊው ከትላንት በስቲያ በማሪዮት ሆቴል ለጋዜጠኞች በሰጠው መግለጫ፤አልበሙ በአይቲውስ እና በአማዞን ከፊታችን ረቡዕ ጀምሮ በይፋ እንደሚለቀቅ ጠቁሞ፣ አዲሱ አልበም  10 ሙዚቃዎችን ማካተቱንና ሦስቱ የቪዲዮ ክሊፕ እንዳላቸው አመልክቷል፡፡ በዚህ አለም አቀፍ ጥራቱን የጠበቀ ነው በተባለለት የሙዚቃ አልበም ላይ በአጃቢነት ከተሳተፉ ታዋቂ ድምፃዊያን መካከል ሱራፌል ፣ ካስማሰ ፣ ቃል ኪዳን ፣ ኩል ሱሬ እና እዮቤድ ይገኙበታል ተብሏል፡፡ በቅንብርና በሚክሲንግ ቢግ ባድ ሳውንድ እንደተሳተፉበት ታውቋል፡፡


 በአይሁዳውያን የሚነገር የአንድ ብልጥ አይሁድ አፈታሪክ እንዲህ ይላል።
አንድ ጊዜ አንድ ህጻን ልጅ በአንድ አይሁዳውያን መንደር ሞቶ ይገኛል። የመንደሩ አይሁዳውያን ተጠሪ የግድያ ተጠርጣሪ ይሆንና ፍርድ ቤት ይቀርባል። ጥፋተኛ ሆኖ ከተገኘም እንዲቃጠል ይወሰናል።
ዳኛው አይሁዳውያንን አይወዱም። ስለዚህ በአደባባይ እንዲህ አሉ፤ ወደሰማይ እየተመለከቱ፤
“እንግዲህ ፍርድ የአምላክ ነው። ሁለት ወረቀቶች ላይ እጣ እጽፋለሁ። “ወንጀለኛ” እና “ከጥፋት ነጻ” አይሁዱ “ወንጀለኛ” የሚለውን ካወጣ እንዲቃጠል ተፈረደበት ማለት ነው። “ከጥፋት ነፃ” የሚል የሚለውን ካወጣን በነጻ ይለቀቃል ማለት ነው።” አሉ።
ዳኛው ይህን ካሉ በኋላ ግን በልባቸው አይሁዱ በምንም አይነት ነጻ የማይወጣበትን ዘዴ እየፈለጉ ነበር። ማንም እንደማይጠረጥራቸው እርግጠኛ ነበሩ። ያገኙት ዘዴ በሁለቱም እጣ ወረቀት ላይ “ወንጀለኛ” የሚል መጻፍ ነበር። ጻፉና ሳጥኑ ውስጥ ከተቱ።
አይሁዱ ወደ እጣ ማውጫው ሳጥን እንዲመጣ ተጠራ። አይሁዱ ግን ዳኛውን ጠርጥሯቸዋል። ስለዚህ እሱም በበኩሉ ዘዴ ሲያጠነጥን ቆይቶ ኖሯል።
ከሳጥኑ ውስጥ አንዱን የተጠቀለለ እጣ አውጣና ሳይገለጥ በፊት እንደተጠቀለለ ወደ አፉ ከተተና በፍጥነት አኝኮ ዋጠው።
ዳኛው አይናቸው ፈጠጠ። ደነገጡ።
“ይሄ ምን ማለት ነው? ምንድን ነው ነገሩ?” ሲሉ ጠየቁ።
“ነገሩ ቀላል ነው። ሳጥኑ ውስጥ የቀረውን እጣ በማየት ወንጀለኛ መሆን አለመሆኑን ማወቅ ይቻላል” ሲል  ሀሳቡን ገለጸ። የቀረው እጣ  ይታይ በሚለው ላይ ተስማሙ። በኋላም ሳጥኑ ውስጥ ያለው እጣ ወጣ። ተገልጦ ሲታይ “ወንጀለኛ” ይላል። ዳኛው “ይሄዋ ወንጀለኛ ነህ” አሉት።
አይሁዱ፤ “ወንጀለኛ አይደለሁም። ምክንያቱም ይሄ ማለት እኔ የዋጥኩት “ከጥፋት-ነጻ” የሚለውን እጣ ነው ማለት ነው። ስለሆነም መፈታት ይገባኛል” ሲል አብራራ። ዳኛው ምንም ሰበብ ፈጥረው ወንጀለኛ ሊደርጉት ባለመቻላቸው እንዲለቀቅ ወሰኑ።

ያላግባብና በጥላቻ “ጥፋተኛ ነህ” የመባል አደጋ ሊኖር እንደሚችል መጠራጠር ተገቢ ነው። በቀላሉ ለመገመት እንደሚቻለኝው፤ ማንም የባላንጣውን ትክክለኛ መልስ የማረጋገጥና አበጀህ የማለት ቀናነት የለውም። በተለይም ድክመቱን የሚያሳይ ገጽታውን አይፈልገውም።
ከስር መሰረቱ ጥፋቱን እንጂ ልማቱን የማይፈልጉ ባላንጣን ምንም ቀዳዳ ሊሰጡት አይሹም። ይልቁንም ህይወቱን አደጋ ላይ “ወንጀለኛ” ብሎ ጽፎ መገላገልን ይመርጣሉ።
አንዳንድ ጊዜ ንጹህና ሀቀኛ መሆን ብቻ ሳይሆን ብልህ መሆንን እንደሚያሻ መገንዘብ አስፈላጊ ነው። የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች ቢበዛ ብልህነት ቢያንስ ደግሞ ብልጠነት እንደሚያጡ ልብ ማት አለብን። በሁለቱም እጣ ወንጀለኛ ላለመሆን አንዱን በንጥሩ ለመጨበጥ የረባ እርምጃና አስተሳሰብ ያስፈልጋል። ለዚህ ደግሞ ያረጀ ልማድና የአመለካከት ዘዴን መለወጥ ዋና ጉዳይ ሆኗል። የምትበድለውን ማወቅ ከበቀሉ ያድንሃል። “አትዋልባት እንዳትውልብህ፣ አትሳላት እንዳታርድህ” እንዲል መጽሐፈ-ምሳሌያዊ አነጋገር። ጭፍን ጥላቻ በየትም መልኩ ቢመጣ የሀገራችን ጠላት ነው። ከኔ ካልሆንክ ከጠላቴነህ ላይ የከፋ ጽንፉ የመሆኑን ያህል ከእኔ ጋር ቆይተህ ድክመት ከታየብህም የጠላቴን ፖለቲካ አጠናክረሃል ማለትም ያው የተሳሳተ ድምዳሜ ነው። ዞሮ ዞሮ ከጠላት የመፈረጃ መካከለኛ ሞገድ ነው። በወጉ በመደራጀት በመብዛትና በመባዛት ፓርቲን ማጠናከር ዋና ነገር ነው። “አትጎብዙ ማለት ነው እንጅ እርግማን አትባዙስ እርግማን አይደለም” የሚለውን ተረት ልብ እንበል። “ጠንካራ ተቃዋሚ ይስጠን” ማለት ጥሩ ጸሎት ነው። ተቃዋሚ እንዳይጠናከር እንቅፋት መፍጠር ግን ከሃጥያት አንዱ ነው። ተቃዋሚው አልጠነክር ማለቱ የራሱ ችግር ነው ማለት ክፉ ነገር አይደለም። ሆን ብሎ የሚበተንበትን መንገድ መተለም ግን ይሁነኝ ብሎ ወደ ጥፋት ማምራት ነው።
ከአንድ ተቋም፣ መ/ቤት የፖለቲካ ፓርቲ፣ ድርጅት ወይም ፓርቲ፣ በማናቸውም መዘዘኛ ግለሰቦችን ወይም ቡድኖችን ለመቀነስ/ለማስወገድ እርምጃ መውሰድ (ዱሮ ሌኒን Purging is purfying ይለው ነበር)/ ማባረር ማጥራት ነው እንደማለት ነው/ በደፈና ሲያዩት ቀላል ይመስላል። በውስጡ ያዘለው ነገር ግን ውስብስብ ነው። ቢያንስ ሶስት ነገሮችን ያዝላል፡-
1ኛ/ በማን ይተኳል 2ኛ/ ልምዱን በምን ያካክሰዋል? 3ኛ/ በእድሜ ብቻ የሚበለጽገው ብስለት ከወዴት ያመጣዋል? ከዚህ በተረፈ ግን ያ የተወገደ ወይም የተባረረ ግለሰብ ቡድን ወዴት ይሄዳል፣ ከማን ይወዳጃል? ድንገት ከባላንጣ ቢወግን ምን አይነት መከላከያ አለ? ወዘተ በታሪክ ሆኖ ዛሬ ተቋሞቻችን፣ ፓርቲዎቻችን መፍትሄ ያላበጁላቸው፣ ዝግጅት የማያደርጉባቸው ክስተቶች ናቸው። የፖለቲካ ሃይል መመናመን፣ መሰነጣጠር፣ ተከፋፍሎም የእኔ ሃይል የሚያክል የታለ ብሎ በባዶ መኩራራት፣ ከእኔ የወጣ ከሀዲ ከእኔ ጋር ያለው ሀቀኛ ቢኖር ፍጹም ማለት ወዘተ ብርቱ ጉድለቶቻችን ተደጋጋሚ ድክመቶችን ናቸው። እነዚህን ሁሉ የሚያካትትልን ደግሞ ወደሌላ የምንልከው ውንጀላ ወደሌላው የምንለኩሰው ጥይት መልሶ ራሳችንን ሊያጠፋን እንደሚችል ማሰባችን ነው። ሁሉም የጊዜ ጉዳይ ነዋ!  ፈረንጆች ወደፊት ተወርውሮ መልሶ ወደራስ መጥቶ የሚወጋ ቀስት/ሹል እንጨት ቡመራንግ ይሉታል (Boomerang):: ከዚህ መዳን አለብን። ቀስቱን ሰትረን ከመቀሰታችን በፊት አላማችንንና ግቡን በውል ማጤን አለብን። የምንፈልገውን በፍትሃዊነት መመዘን አለብን።
በዚህ መንፈስ ዛሬን በጋራ እናስብ፣ እንስራ፣ በዓላችንን እናክብር። መልካም የልደት በዓል፡፡



Wednesday, 03 January 2024 20:37

መላ

መላ

የአለምን ጫጫታ ላፍታ ለማስታገስ
ሆድ ውስጡን ባሰሰ፤
ላገኘ በልቡ የህሊና ጩኸት
ከውጩ የባሰ፤
ልቡን ከሆዱጋ'፥ ላልቻለ ማስማማት
በበደል ተከ'ባ፥ ነፍሱን ለደከማት
.
ኑሮ ትግል ጣጣው፥
ንዋይ እድል እጣው፥
ሁሉም ግራ ሆኖ መሄጃ ላሳጣው፤
.
ጊዜ ነው አቃፊው፥
መጥፎን ከጥሩጋ' አጣምሮ አሳላፊው፤
.
ዝምታው ነው ጌታ፥
የጭንቀት ወራትን ባ'ርምሞ 'ሚረታ፤
.
ተስፋ ነው መድሀኒት፥
የነገን ሁኔታ ዛሬ ላይ 'ሚገምት፤
.
ፍቅር ነው መካሪው፥
ውሸትን ገፍትሮ ለእውነት መስካሪው፤
እምነት ነው አዛኙ፤
ጥፋትን ሳይቆጥር የልብን መዛኙ።
✍️ Sami Anteneh]

ዳሽን ባንክና የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ደንበኞች የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ተጠቅመው ክፍያውን ቆይተው የሚከፍሉበትን ‘ጉዞዎ ይቀድማል ክፍያው ይደርሳል’ የተሰኘ አዲስ የክፍያ አማራጭ አገልግሎት ከትላንት በስቲያ ሐሙስ በጋራ አስተዋውቀዋል፡፡  
የዳሽን ባንክ ዲጂታል ባንኪንግ ዋና መኮንን አቶ ዮሐንስ መኮንን እንደገለጹት፤ ‘ጉዞዎ ይቀድማል ክፍያው ይደርሳል’ የተሰኘው አዲሱ  የክፍያ አማራጭ  በደንበኞች ምርጫ መሰረት በ6 ወር ወይም በ12 ወር የብድር ክፍያ የሚሰጥ ነው፡፡  ደንበኞች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ለመሆን በዳሽን ባንክ የሂሳብ ቁጥር መክፈት እንደሚገባቸውና በተጨማሪም በባንኩ ቢያንስ ለሦስት ወራት አገልግሎት ያገኙ መሆን እንደሚገባቸውም አመልክተዋል፡፡
አዲሱን አገልግሎት ለመጠቀም አንድ ደንበኛ አስፈላጊ ቅድመ-ሁኔታዎችን ካሟላ በኋላ በቅርንጫፉ የተፈቀደለትን የብድር መጠን የሚወስድ ሲሆን፤ የተፈቀደለትን ገንዘብ ለመጠቀም የሚያስችል የአንድ ጊዜ መለያ ቁጥር መልዕክትም በተንቀሳቃሽ ስልኩ የሚደርሰው ይሆናል።
 በመቀጠልም ደንበኛው የተሰጠውን መለያ ቁጥር በአየር መንገዱ የሞባይል መተግበሪያ ላይ በማስገባት ትኬት መቁረጥና የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆን ይችላል።
በሁለቱ ተቋማት ስምምነት በቀረበው በዚህ አገልግሎት ተጠቃሚ ለመሆን የሚፈቀደው የብድር ገንዘብ መጠን እስከ ስድስት መቶ ሺ ብር የሚደርስ ነው። የሚፈቀደው ብድር ወለድ የሚታሰብበት ሲሆን፤ ይህም ደንበኛው በመረጠውና ብድሩን በወሰደበት የጊዜ ገደብ ከብድሩ ጋር አብሮ የሚከፈል መሆኑ ተጠቁሟል፡፡
የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና የንግድ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ለማ ያዴቻ በበኩላቸው፤ “የኢትዮጵያ አየር መንገድ ደንበኛ ተኮር አሰራርን እንደመከተሉ የተለያዩ ዘመናዊና ለመጠቀም ቀላል የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን እያስተዋወቀ ይገኛል። የምናበለጽጋቸው ቴክኖሎጂዎች ለደንበኞቻችን ምቹ መሆናቸው እንደተጠበቁ ሆኖ የአገር ውስጥ የፋይናንስ ተቋማት ከሚሰጡት አገልግሎት ጋርም የተጣጣሙ እንዲሆኑ እናደርጋለን። ዛሬም አጋራችን ከሆነው የዳሽን ባንክ ጋር በመተባበር ለደንበኞቻችን ያቀረብነው አዲስ የክፍያ አማራጭ ተግባራዊ እንዲሆን የሞባይል መተግበሪያችን ከአዲሱ የክፍያ አገልግሎት ጋር የተቀናጀ እንዲሆን አድርገናል” ብለዋል።
ደንበኞች የተፈቀደላቸው የብድር መጠን ሲያልቅ ማደስ የሚችሉ ሲሆን፤ በአንዴ የወሰዱትን ብድርም ለተለያዩ በረራዎች ከፍለው መጠቀም እንደሚችሉ ታውቋል፡፡  አገልግሎቱ በተለይም በንግድ ስራ ላይ ለተሰማሩ ጅምላ አስመጪዎችና ለዕረፍት ከቤተሰቦቻቸው ጋር ወደ ውጭ ለሚሄዱ ደንበኞች አመቺ ነው ተብሏል።

 በሃዋሳ ከተማ በምሥራቅ ክፍለ ከተማ በ280 ሚሊዮን ብር ወጪ በ700 ካ.ሜ ቦታ ላይ የተገነባው ባለ 3 ኮከቡ ፌኔት ሆቴል፣ ታህሳስ 13 ቀን 2016 ዓ.ም  የክልሉ የሥራ ሃላፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡ የዕለቱ የክብር እንግዳ የሲዳማ ክልል ፕሬዚዳንት አማካሪ አቶ ተሰማ ዲማ በምርቃት ሥነስርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር፤ “ሃዋሳ የቱሪዝም ከተማ እንደመሆኗ ሆቴሉ ትልቅ አስተዋፅኦ ያበረክታል” ብለዋል።
አዳዲስና ዘመናዊ አገልግሎቶችን ያካተተው ፌኔት ሆቴል፤ የኮንፍረንስ ቱሪዝሙን መደገፍ የሚችሉ የተለያዩ አገልግሎቶችን የሚሰጡ ክፍሎች ጭምር የያዘ ነው ተብሏል፡፡ለ41 ቋሚና 10 ጊዜያዊ ሰራተኞች የሥራ ዕድል ፈጥሯል የተባለው ሆቴሉ፤ የከተማዋን የቱሪስት እንቅስቃሴና ገቢ ለማሳደግ የላቀ አስተዋጽኦ እንደሚያደርግ ተነግሯል፡፡
በ1992 ዓ.ም በሃዋሳ ከተማ ጥቂት ሰራተኞችን ይዞ በ50ሺ ብር በጀት በኪራይ ቤት የተጀመረው ሥራ፣ ለረዥም ዓመታት በከተማዋ ተወዳጅ ሆኖ ወደዘለቀው ፌኔት ክትፎ ቤት እንዳደገና  አሁን ደግሞ ባለ 3 ኮኮብ ሆቴል ማዋለድ እንደቻለ በምረቃ ሥነስርዓቱ ላይ ተጠቁሟል፡፡  ፌኔት ሆቴል፤ በቀጣይ  ባለ 4 ኮኮብ ሆቴል ለመገንባት ያቀደ ሲሆን፤ ለክልሉ የመሬት ጥያቄ አቅርቦ ምላሽ እየጠበቀ እንደሚገኝ የሆቴሉ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጤናዬ ዋርጌ ተናግረዋል፡፡

  ንብ ኢንተርናሽናል ባንክ፤ በሃዋሳ ፒያሳ በ500 ሚሊዮን ብር ያስገነባውን ባለ 12 እና ባለ 15 ወለል መንትያ ህንፃ ባለፈው ቅዳሜ ነሐሴ 13 ቀን 2016 ዓ.ም የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በተገኙት አስመርቋል፡፡
የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ አዲሱን ህንፃ ከጎበኙ በኋላ ባደረጉት ንግግር፤ “ንብ ባንክ በሲዳማ ክልልም ሆነ በሃዋሳ ከተማ አስተዳደር ተጨማሪ ኢንቨስትመንት ማስፋፋት ለሚያቅዱ ሌሎች አካላት ምሳሌ የሚሆን  ተግባር እያከናወነ ነው፡፡” ብለዋል፡፡
ህንፃው ከአንደኛ እስከ ሦስተኛ ወለል የተለያዩ ሱቆች፣ ከአራት እስከ ስምንተኛ ወለል የሚከራዩ ቢሮዎች ያሉት ሲሆን፤ ዘጠነኛ ወለል ላይ የባንኩ ሃዋሳ ዲስትሪክት ፅ/ቤትና ከአንድ መቶ ሰዎች በላይ ሊያስተናግድ የሚችል አዳራሽ ይዟል፡፡ በተጨማሪም በአስረኛ ወለሉ ላይ የማረፊያ ክፍሎች ያሉት ሲሆን፤ አስራ አንደኛው ወለሉ ላይ ደረጃውን የጠበቀ ሬስቶራንት እንደያዘ ለማወቅ ተችሏል፡፡
 የንብ ኢንተርናሽናል ባንክ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ገነነ ሩጋ በምረቃው ሥነስርዓት ላይ ባደረጉት ንግግር፤ “ንብ ባንክ፣ በባንክ አገልግሎቱ በበርካቶች ዘንድ ተደራሽ ከመሆኑ በተጨማሪ በአገሪቱ በተለያዩ ከተሞች ህንፃዎችን አስገንብቶ ሥራ ላይ በማዋሉ ከራሱ ባሻገር ለአገሪቱ ኢኮኖሚ ግንባታ እንዲሁም ለብዙዎች የሥራ እድል በመፍጠር ረገድ የበኩሉን አስተዋፅኦ በማበርከት ላይ ይገኛል፡፡ ባንካችን ህብረተሰቡን ተጠቃሚ ለማድረግ በቀጣይም ይህን ጥረቱን አጠናክሮ የሚቀጥል መሆኑን በዚህ አጋጣሚ ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ፡፡” ብለዋል፡፡
ባንኩ ከዚህ ቀደም ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በወልቂጤ፣ በዱከምና በሆሳእና የዋና መሥሪያ ቤት ህንፃዎችን ማስገንባቱ ይታወቃል፡፡

በአንድ አፈ-ታሪክ ውስጥ የሚገኝ የስድስት ሰዎችና የአንድ ትእቢተኛ ንጉሥ ታሪክ አለ፡፡ እንዲህ የሚል፡፡ አንድ መልካም እውቀት ያለው፣ አገሩን ከልቡ የሚወድና በሰራዊቱ ውስጥ በጀግንነት ያገለገለ ጎበዝና ብልህ ወታደር ጦርነቴ እንዳበቃ ለመጓጓዣ ያህል ብቻ ፍራንክ ሰጥቶ፤ ትእቢተኛው ንጉሥ ያባርረዋል፡፡
ወታደሩ በጣም አዝኖ “ንጉሱ እንዴት እንዲህ ጉድ ይሰሩኛል? እኔን የሚመስሉ ሰዎች ፈልጌ፣ እኒህን ንጉስ ያለ የሌለ ሀብታቸውን እንዲያስረክቡኝ አድርጌ ሙልጭ አወጣቸዋለሁ!” ብሎ ዝቶና ተቆጥቶ በእልህ ካገሩ ይወጣል፡፡
 ከዚያም በአንድ ጫካ ውስጥ እየተጓዘ ሳለ አንድ እጅግ በጣም ግዙፍ ሰውዬ ሳር የሚያጭድ ይመስል በተአምረኛ እጁ የጫካውን ግንድ ሁሉ እየገነደሰ ሲሸከም ያገኘዋል፡፡ “ወዳጄ ኃይል ጉልበት አለህና ለምን አብረን ሆነን ችሎታችንን አቀናጅተን በዓለም ውስጥ የተሳካላቸው ሁለት ሰዎች አንሆንም?” ብሎ ይጠይቀዋል፡፡ ግዙፉ ሰው በሃሳቡ ተስማምቶ ተከተለው፡፡
ጥቂት እልፍ እንዳሉ አንድ አነጣጣሪ አዳኝ ያገኛሉ፡፡ አዳኙ “ከስንትና ስንት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ የአንዲትን ትንኝ ግራ ዓይን ለመምታት እያነጣጠርኩ ነው” ይላቸዋል፡፡ “ችሎታችንን ብናቀናጅኮ በአለም ውስጥ ሶስት የተሳካላቸው ሰዎች እንሆናለን፡፡ እባክህ አብረን እንሂድ” አሉት፡፡ እሺ ብሎ ተከተላቸው፡፡ አሁንም እልፍ እንዳሉ አንድ ትልቅ ዛፍ ጫፍ ላይ ወጥቶ የተቀመጠ ሰው ያገኛሉ፡፡ “እዚያ ዛፍ ጫፍ ላይ ተቀምጠህ ምን ታደርጋለህ?” ሲል ጀግናውና ብልሁ ወታደር ጠየቀው፡፡ ሰውዬውም “ከብዙ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ሰባት በንፋስ የሚሰሩ ወፍጮዎች ይታዩኛል፡፡ አቅም አጥተው መሽከርከራቸውን አቁመዋል፡፡ ስለዚህ እነሱን ለማሽከርከር በተአምራዊ ኃይሌ ለመጠቀም አንዱን የአፍንጫዬን ቀዳዳ ደፍኜ በሌላኛው ስተነፍስ ወዲያው መዞር ይጀምራሉ” አላቸው፡፡ “በል ና አብረን እንሂድ፤ እኔ ብልህና ጀግና ወታደር ነኝ፡፡ እነዚህም እንዳንተው ችሎታ ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ አራታችን አንድ ብንሆን አለምን ለማሸነፍ እንችላለን” አለው፡፡ አውሎ ንፋስ ከአፍንጫው ማፍለቅ የሚችለው ሰውም ደስተኛ ሆነ፡፡
ጥቂት እንደተጓዙ በቀኝ እግሩ ብቻ የቆመና ግራ እግሩን ከጉልበቱ ፈትቶ መሬት ያጋደመ ሰው ያገኛሉ፡፡ “እግርህ ተቆርጦ እንዴት ተመችቶህ ቆምህ?” አለና ጠየቀው ብልሁ ጀግና፡፡ “እኔ ከወፎች የበለጥኩ ሯጭ ነኝ፡፡ ሁለቱንም እግሬን ከተጠቀምኩ ንፋስም አይቀድመኝም፡፡ ስለዚህ ረጋ ብዬ ለመሄድ እንድችል አንዱን እግር አውልቄ አስቀምጠዋለሁ” ይላል፡፡ “ተከተለንና አምስታችን ችሎታችንን አቀናጅተን አለምን እናሸንፍ” ይለዋል ብልሁ ጀግና፡፡ ሯጩም ተስማምቶ አብሯቸው ይጓዛል፡፡
 በመጨረሻ መንገድ ላይ ያገኙት አንድ ባርሜጣውን በአንድ ጆሮው ላይ ያንጠለጠለ ሰው ነበር፡፡ እሱም ለምን እንደዚያ እንዳደረገ ሲጠይቁት፣ ባርሜጣውን አስተካክሎ ካጠለቀ በኋላ በአካባቢው ያለውን ነገር ሁሉ እንደበረዶ ማቀዝቀዝ እንደሚችል ነገራቸው፡፡ “ስድስታችን አንድነት ቢኖረን አለምን እናሸንፋለንና አብረን እንሁን” አለው ብልሁ ጀግና፡፡ በሀሳቡ ተስማምቶ አብረው ሆኑ፡፡
ተሰብስበው ወደ እብሪተኛው ንጉስ ሲሄዱ ንጉሱ አዲስ አዋጅ አውጀው ደረሱ፡፡ አዋጁም “ከሴት ልጄ ጋር ሮጦ ተሽቀዳድሞ ያሸንፈ ባሏ ይሆናል፡፡ ሩጫው ካልተሳካለት ግን እንገቱ ይቆረጣል” የሚል ነበር፡፡ ብልሁ ጀግናም “የእኔ ሯጭ ያለጥርጥር ይቀድማታል” ሲል በኩራት ተናገረ፡፡ ንጉሱም “ቢሸነፍ ግን ያንተ ሯጭ ብቻ ሳይሆን ያንተም የራስህ አንገት ጭምር ይቆረጣል” ሲሉ ያስፈራሩታል፡፡ ውድድሩ ሩቅ ቦታ ወዳለ የውሃ ጉድጓድ ሮጦ ውሃ በባልዲ ቀድቶ ይዞ መምጣት ነው፡፡ የንጉሱ ልጅ እጅግ በጣም ፈጣን ሯጭ ናት፡፡ ንጉሡ ይተማመኑባታል፡፡
ሯጩ እግሩን ገጣጠመና ውድድሩ ተጀመረ፡፡ መቼ ሄደ ሳይባል በንፋስ ፍጥነት ሮጦ ውሃውን ቀዳና ሲመለስ ትንሽ አረፍ ልበል፤ ብሎ መንገድ ላይ ተኛ፡፡ እንዳይዘናጋና ብዙ እንቅልፍ እንዳይወስደው የሞተ ፈረስ የራስ-ቅል አግኝቶ ያንን ተንተራሰ፡፡ ሆኖም እንቅልፍ ይዞት ጭልጥ አለ፡፡ የንጉሱ ልጅ ገና ጉድጓድ እየሄደች ሳለች ተኝቶ አገኘችው፡፡
የሱን ባልዲ ውሃ ወደራሷ ባልዲ ገልብጣ ወደ ቤተመንግስት ገሰገሰች፡፡ ይህን ሁኔታ አነጣጣሪው ተኳሽ አየ፡፡ ስለዚህ በልዩ ችሎታው አነጣጥሮ ሯጩ የተንተራሰውን የፈረስ - ራስ- ቅል ነጥሎ መታው፡፡ ይሄኔ ሯጩ ነቃ፡፡ ባልዲው ባዶ መሆኑን ሲያይ ተንኮሉ ገብቶት እንደ ንፋስ በርሮ ውሃውን ይዞ የንጉሱን ልጅ ቀድሟት ገባ፡፡
ንጉሱ ተናደዱ፡፡ “ለዚህ ለጭባም ልጄን አልሰጥም!” አሉ፡፡ ስለዚህ ሌላ መላ መቱ፡፡ “በሉ የደስ ደስ ብሉ ጠጡ፡፡ ከዚያ ምቹ አልጋ ባለው ክፍል ተኙ፡፡ ጠዋት ልጄን ትረከባላችሁ” ይላሉ፡፡
ስድስቱ መንገደኞች በልተው ጠጥተው ተኙ፡፡ ለካ የተኙበት ቤት ከብረት የተሰራና በሩ ከተዘጋ መውጫ የሌለው ኖሯል፡፡ የንጉሱ አሽከር ከቤቱ ስር ካለው ምድር-ቤት ሆኖ እሳት ከስር እንዲያነድድና በብረቱ ግለት ታፍነው እንዲሞቱ ትእዛዝ ተቀብሎ ኖሮ እሳቱን ለቀቀባቸው፡፡ ሆኖም ባለባርሜጣው ጓደኛቸው ተንኮሉ ስለገባው ባርሜጣውን አስተካክሎ ሲያደርገው ብረቱ ሁሉ እንደበረዶ ቀዘቀዘና እሳቱም ሊያቀልጠው አልቻለም፡፡
ጠዋት ንጉሱ መጥተው ሲያዩ ስድስቱ ጓደኛሞች በሰላም ሲስቁ ሲጫወቱ አገኟቸው፡፡ በገኑ!! ጮሁ!! በንዴት አሽከራቸውን ትዕዛዜን አልፈፀምክም በሚል እንዲገደል አደረጉ፡፡
ሊሸነፉ መሆናቸውን ሲያውቁም ብልሁን ጀግና ጠርተው “በልጄ ፈንታ የፈለግኸውን ጠይቀኝ አደርግልሃለሁ!” አሉት፡፡ ብልሁ ሰውም “አሽከሬ ሊሸከመው የሚችለውን ያህል ወርቅ ይስጡኝ” አላቸው፡፡ ንጉሱ በጣም ተደሰቱ፡፡ “አሽከርህ መሸከም ካልቻለ ግን ሀብቴን ትመልሳለህ፡፡ በዚህ እንስማማ” አሉት፡፡ ብልሁ ጀግና ተስማማ፡፡ ንጉሱም ልባቸው ጮቤ ረገጠች፡፡ ከዚያ አንድ ዘዴ ፈጠሩ፡፡ የአገሩን ልብስ ሰፊዎች በሙሉ ሰብስበው ሰው ሊሸከመው የማይችል ትልቅ ከረጢት ስፉ ብለው አዘዙ፡፡
ልብስ ሰፊዎች እንደታዘዙት ትልቅ ድንኳን የሚያህል ከረጢት ሰፉ፡፡ ንጉሱ ያለ የሌለ ዕንቁ፣  ወርቅ ጌጣ ጌጥና ብር ሁሉ እንዲሞላ አዘዙና ተሞልቶ ተዘጋጀ፡፡
ያ የጫካውን ግንድ ሁሉ ሲሸከም የነበረው ግዙፍ ሰው ባንዴ ድንኳን አከሉን ከረጢት አንጠልጥሎ ስድስት ጓደኛሞች መንገድ ጀመሩ፡፡ ንጉሱ ተናደዱ፡፡ እብድ ሆኑ፡፡ አይኔ እያየ ምድረ-አቅመ ጎዶሎ፣ ምድረ-ጭባ ሀብቴን አይወስድ ብለው ፈረሰኛ ወታደሮች ሄደው፣ ስድስቱን መንገደኞች ገድለው ወርቁን ይዘው እንዲመጡ በቁጣ ያዝዛሉ፡፡
ፈረሰኞቹ ስድስቱ ተጓዦች ጋ ደርሰው፤ “እጅ ወደላይ!! በሰላም ሀብቱን አስረክቡ! አለዚያ እንጨርሳችኋለን!” ይሏቸዋል፡፡
በዚህን ጊዜ ከአፍንጫው አውሎ-ንፋስ ለማውጣት የሚችለው ተጓዥ፣ አንዱን የአፍንጫውን ቀዳዳ በእጁ ይዞ አንዴ ሲተነፍስ ወታደሮቹ ከእነ ፈረሳቸው ድምጥማቸው ጠፋ!
ንጉሱ የሆነውን ሁሉ ሲሰሙ በንዴት የቤተ-መንግስቱን ሰው ሁሉ በትንሽ በትልቁ ሰበብ አንገቱን እየቆረጡ የቅርብ ወዳጆቻቸውን ሳይቀር እየተነኮሱ፣ ጠበ -እየጫሩ ገድለው ጨረሱ፡፡
በመጨረሻም በነገሥኩበት አገር ውርደት አላይም ብለው ወደሌላ አገር ተሰደዱ፡፡ በተሰደዱበት አገር ሳሉ አእምሯቸው ተነካ፡፡ ይሄው እስከዛሬ ከእንቅልፋቸው በባነኑ ቁጥር “ልጄን ለማንም ጭባ አልሰጥም!” እያሉ ይጮሃሉ!!
***
ለአገሩ ለህዝቡ የሰራ የማይገፋባት፣ የማይገለልባት የማይበደልባት አገር ታስፈልገናለች፡፡ መሪ አለቃ ሃላፊ እብሪት ሲጠናወተው የማይታይባት አገር ታሻናለች፡፡ አቅማቸውን አቀናጅተው ለመስራት ለውጥ ለማምጣት የሚጥሩ “ተአምረኛ” ልጆች ያሉዋት አገር የታደለች ናት፡፡ በዋና ጉዳይ በድሎ በአናሳ ጉዳይ የሚያባብል የማይኖርባት አገር መልካም ቤት ናት፡፡ “ራሴን መትቶኝ እግሬን ቢያክልኝ ምንም አይገባኝ” የማይባልባት አገር ብትኖረን እንፀድቃለን፡፡ ሀገራችን የቅርብ ወዳጁን የማይንቅ የማይሰድብ፤ የቅርብ አጋሩን የማይርቅ፤ ድንገት ጎህ ቅዳጅ ላይ ዘራፍ የማይል፤ ድንገት ጀንበር መጥለቂያ ላይ ደሞ የማይሸማቀቅ እውነተኛ ሰው በመብራት የምትፈልግበት ዘመን ነው፡፡ ህዝብና አገር መሳለቂያ እንዳይሆኑ ስለእውነታቸው ከልብ የሚሟገቱ፣ ፈጠንኩ ብሎ የተመነጠቀውን ተመለስ ለማለት የሚደፍሩ፤ እየተራመደ መስሎ የሚያነክሰውን ወይ ዝለቅ ወይ ራቅ ለማለት የማይራሩ፤ የፈረደ መስሎ የሚሞዳሞደውን ውረድ ለማለት አይናቸውን የማያሹ ደመ መራራ ሹማምንት እንደሚያስፈልጉ ሁሉ ከአሻንጉሊትነት ነፃ የሆኑ ዲፕሎማሲን ግን የተካኑ ልባቸው ያልተደፈነ አእምሯቸው ያልተሸፈነ፣ እንቅፋት በመታቸው ቁጥር “መድኃኒት አድርገውብኝ ነው” የማይሉ፤ አለቃ ባስነጠሰ ቁጥር “መፈክር ይማርህ!” ብለው የማያላዝኑ ልባም ሰዎች የሚፈለጉበት ሰዓት ነው፡፡ ጉልበት እብሪት ንፉግነት ፣ ‘እኔ ብቻ አዋቂ’ ማለት፤ ‘እጁን ያወጣ ወዬለት’ ማለት ወደ ሰላም ሳይሆን ወደ ግጭት፤ ወደ መቀራረብ ሳይሆን ወደሽሽት የሚያመራ ነው፡፡ በዚሁ ፈር የልባቸውን ለመናገር ድፍረት ያጡ እየበረከቱ ከመጡ “ብትር ፈርተን ነው እንጂ የናቶቻችንን መዋያማ እናውቀዋለን” አለች ጥጃ የሚሉ ሰዎች የምናፈራባት አገር ብቻ ናት የምትኖረን፡፡
አንድ ጊዜ አንድ አዋቂ “ሞተር ብስክሌተኛ ማለት ምን ማለት ነው?” ተብሎ ሲጠየቅ የሚሄድ ሰው ነው” ብሎ ነበር፡፡ የሰማነውን በየልቦናችን ያሳድርልን፡፡

ቶሞካ ቡና ኃ.የተ.የግል.ማህበር በንኮማድ ኮንስትራክሽን ኃ.የተ.የግል ማህበር (ደንበል ሲቲ ሴንተር) ላይ የ48.2 ሚሊዮን ብር ክስ መመስረቱ ታወቀ፡፡
ከሳሽ ቶሞካ ቡና ጥር 7 ቀን 2011 ዓ.ም ስፋቱ 137 ካሬ ሜትር የሆነውንና በደንበል ሲቲ ሴንተር ህንፃ ላይ የሚገኘውን ቦታ እስከ ጥር 6 ቀን 2021 ዓ.ም ለአስር ዓመት ለቡና መሸጫ ካፊቴሪያነት አገልግሎት ለማዋል ከንኮማድ ኮንስትራክሽን ጋር የኪራይ ውል መዋዋሉን የክስ ጭብጡ ያስረዳል፡፡ ከሳሽ በዚሁ ውል መሰረት በመጋቢት ወር 2011 ዓ.ም በተፈፀመ የግንባታ ውል ቦታው ለቡና መሸጫነት ምቹና ደረጃውን የጠበቀ እንዲሆን 1 ሚሊዮን 491 ሺህ 403 ብር ወጪ በማድረግ አድሶና አሳምሮ ስራውን መቀጠሉን ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት፣ ልደታ ምድብ ችሎት፣ የውል ጉዳዮች ችሎት የቀረበው የክስ መዝገብ ያመለክታል፡፡
ይሁን እንጂ ተከሳሽ ጥቅምት 19 ቀን 2016 ዓ.ም በተፃፈ ደብዳቤ የኪራይ ውሉ መቋረጡን በመግለፅ  ካፌው የሚጠቀምበትን የኤሌክትሪክ የመብራት መስመር በማቋረጥና አገልግሎት እንዳይሰጥ በማድረግ በድርጅቱ ላይ ከፍተኛ ኪሳራ ማድረሱን ከሳሽ ለፍ/ቤቱ ባቀረበው ክስ አመልክቷል፡፡
ተከሳሽ     ውሉን ያቋረጠባቸው ምክንያቶች ከህግና ከስነስርዓት ውጪ በመሆናቸውና ለኪሳራ ስለዳረገኝ ፍርድ ቤቱ ይህን ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ ተከሳሽ 48 ሚሊዮን 272 ሺህ 360 ብር እንዲከፍለኝ እንዲወስንልኝ ሲል መጠየቁን የክስ ዝርዝሩ ያስረዳል፡፡
በጉዳዩ ላይ አስተያየት እንዲሰጡን በስልክ የጠየቅናቸው የንኮማድ ኮንስትራሽን ኃ.የተ.የግል ማህበር ስራ አስኪያጅ አቶ አበበ መንገሻ “በስልክ ምንም አይነት ምላሽ አልሰጥም” በማለታቸው ምላሻቸውን ማካተት አልቻልንም፡፡

 (የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ጋዜጣዊ መግለጫ)

          የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)፤ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል፣በጉራጌ ዞንና በቀቤና ልዩ ወረዳ መካከል የነበረውን አለመግባባት ተከትሎ ጥቅምት 2 ቀን 2016 ዓ.ም. ጀምሮ የተከሰተውን የጸጥታ መደፍረስና ያስከተለውን ጉዳት ከአካባቢው ነዋሪዎች በቀረበለት አቤቱታ መነሻነት ከጥቅምት 20 እስከ 25 ቀን 2016 ዓ.ም.በቦታው በመገኘት ጭምር ምርመራ ያከናወነ ሲሆን፣ አሁንም በአካባቢው ያለውን አጠቃላይ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታም በመከታተል ላይ ይገኛል፡፡ ኮሚሽኑ ከተጎጂዎችና ምስክሮች ጋር 22 ቃለ-መጠይቆች አድርጓል፤ ከጉራጌ ዞን፣ ከወልቂጤ ከተማ አስተዳደርና ከቀቤና ልዩ ወረዳ የሥራ ኃላፊዎች፣ በዞንና በልዩ ወረዳ ደረጃ ከሚገኙ የመንግሥት ኃላፊዎች እንዲሁም በአካባቢው የሚገኘውን የኮማንድ ፖስት ኃላፊዎችን አነጋግሯል፤ ከሃይማኖት መሪዎችና ከሀገር ሽማግሌዎች ጋር 2 የቡድን ውይይቶች አካሂዷል፡፡ በተጨማሪም ዘረፋና ውድመት ደርሶባቸዋል የተባሉ የግልና የመንግሥት ተቋማትን ተዘዋውሮ ጎብኝቷል፤ተጎጂዎች ሕክምና ካገኙባቸው የሕክምና ተቋማት ማስረጃዎችን ጨምሮ የተለያዩ የሰነድ ማስረጃዎችን አሰባስቧል።
በጉራጌና በቀቤና ማኅበረሰብ መካከል ከዚህ በፊትም የተለያየ መጠን ያለው ግጭትና የሰላም ስምምነት ጥረት የነበረ ሲሆን፤ በተለይ ከቀቤና የልዩ ወረዳነት ምሥረታ ጋር በተያያዘና የልዩ ወረዳው መቀመጫን በተመለከተ በሁለቱ ማኅበረሰቦች አስተዳደሮች መካከል አለመግባባቱ እየተካረረና የግጭት አደጋው እየጨመረ መጥቶ እንደነበር መረዳት ተችሏል።
የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ፤ “በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልልም ሆነ በሌሎች አካባቢዎች አሁንም ዘላቂ መፍትሔ ያልተሰጣቸው የመዋቅርና የአስተዳደር ጥያቄዎች ለሰላምና ደኅንነት እጦት እንዲሁም ለሰብአዊ መብቶች ጥሰት ምክንያት ሆነው መቀጠላቸው እጅግ አሳሳቢ ስለሆነ፤ የፌዴራልና የክልል መንግሥታት ኃላፊዎች ቅሬታና ጥያቄ የቀረበባቸውን አካባቢዎች ሁሉ ተዓማኒ በሆነና ተቀባይነት ባለው ሂደት በማሳተፍ ዘላቂ መፍትሔ ሊያመቻቹ ይገባል” ብለዋል፡፡
ዋና ኮሚሽነሩ አክለውም፤ “በወልቂጤ ከተማ ጥቅምት 2 ቀን 2016 ዓ.ም. ጀምሮ የተከሰተውን ሁከትና የደረሰውን ጉዳት በተመለከተ የክልሉና የፌዴራል መንግሥት በመቀናጀትና ተገቢውን ማጣራት በማድረግ ተጠያቂነትን ማረጋገጥና ተጎጂዎችን መካስ ይገባል” ብለዋል፡፡



‘Fly Now Pay Later’


 ዳሽን ባንክና የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ደንበኞች የአየር ትራንስፖርት አገልግሎት ተጠቅመው ክፍያውን ቆይተው የሚከፍሉበትን ‘ጉዞዎ ይቀድማል ክፍያው ይደርሳል’ የሚል  አዲስ የክፍያ አማራጭ በዛሬው ዕለት አስተዋወቁ።

የዳሽን ባንክ ዲጂታል ባንኪንግ ዋና መኮንን አቶ ዮሐንስ መኮንን እንደገለጹት፤ ‘ጉዞዎ ይቀድማል ክፍያው ይደርሳል’ የተሰኘው አዲሱ  የክፍያ አማራጭ  በደንበኞች ምርጫ መሰረት በ6 ወር ወይም በ12 ወር የብድር ክፍያ የሚሰጥ ነው፡፡

 ደንበኞች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ለመሆን በዳሸን ባንክ የሂሳብ ቁጥር መክፈት እንደሚገባቸውና በተጨማሪም በባንኩ ቢያንስ ለሦስት ወራት አገልግሎት ያገኙ መሆን እንደሚገባቸውም አመልክተዋል፡፡

አዲሱን አገልግሎት ለመጠቀም አንድ ደንበኛ አስፈላጊ ቅድመ-ሁኔታዎችን ካሟላ በኋላ በቅርንጫፉ የተፈቀደለትን የብድር መጠን የሚወስድ ሲሆን፤ የተፈቀደለትን ገንዘብ ለመጠቀም የሚያስችል የአንድ ጊዜ መለያ ቁጥር መልዕክትም በተንቀሳቃሽ ስልኩ የሚደርሰው ይሆናል። በመቀጠልም ደንበኛው የተሰጠውን መለያ ቁጥር በአየር መንገዱ የሞባይል መተግበሪያ ላይ በማስገባት ትኬት መቁረጥና የአገልግሎቱ ተጠቃሚ መሆን ይችላል።

በሁለቱ ተቋማት ስምምነት በቀረበው በዚህ አገልግሎት ተጠቃሚ ለመሆን የሚፈቀደው የብድር ገንዘብ መጠን እስከ ስድስት መቶ ሺ ብር የሚደርስ ነው። የሚፈቀደው ብድር ወለድ የሚታሰብበት ሲሆን፤ ይህም ደንበኛው በመረጠውና ብድሩን በወሰደበት የጊዜ ገደብ ከብድሩ ጋር አብሮ የሚከፈል መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና የንግድ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ለማ ያዴቻ በበኩላቸው፤ “የኢትዮጵያ አየር መንገድ ደንበኛ ተኮር አሰራርን እንደመከተሉ የተለያዩ ዘመናዊና ለመጠቀም ቀላል የሆኑ ቴክኖሎጂዎችን እያስተዋወቀ ይገኛል። የምናበለጽጋቸው ቴክኖሎጂዎች ለደንበኞቻችን ምቹ መሆናቸው እንደተጠበቁ ሆኖ የአገር ውስጥ የፋይናንስ ተቋማት ከሚሰጡት አገልግሎት ጋርም የተጣጣሙ እንዲሆኑ እናደርጋለን። ዛሬም አጋራችን ከሆነው የዳሽን ባንክ ጋር በመተባበር ለደንበኞቻችን ያቀረብነው አዲስ የክፍያ አማራጭ ተግባራዊ እንዲሆን የሞባይል መተግበሪያችን ከአዲሱ የክፍያ አገልግሎት ጋር የተቀናጀ እንዲሆን አድርገናል” ብለዋል።

ደንበኞች የተፈቀደላቸው የብድር መጠን ሲያልቅ ማደስ የሚችሉ ሲሆን፤ በአንዴ የወሰዱትን ብድርም ለተለያዩ በረራዎች ከፍለው መጠቀም እንደሚችሉ ታውቋል፡፡  አገልግሎቱ በተለይም በንግድ ስራ ላይ ለተሰማሩ፣ ለጅምላ አስመጪዎችና ለዕረፍት ከቤተሰቦቻቸው ጋር ወደ ውጭ ለሚሄዱ ደንበኞች አመቺ ነው ተብሏል።