Administrator

Administrator

Monday, 20 March 2017 00:00

ማረሚያ

    ባለፈው ሳምንት የጋዜጣው ዕትም “በማዕተብ ጉዳይ ከመምህሩ ጋር የተጋጨው ተማሪ ራሱን አጠፋ” በሚል ርዕስ በወጣው ዜና ላይ ተማሪው የጅማ ዩኒቨርሲቲ የመምህራን ኮሌጅ ተማሪ እንደሆነ የተገለፀው በስህተት ሲሆን ተማሪው በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ትምህርት ቢሮ በሚተዳደር “የጅማ መምህራን ኮሌጅ” ይማር የነበረ መሆኑን ለመግለፅ እንወዳለን፡፡ ለተፈጠረው ስህተት ውድ አንባቢያንንና የጅማ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብን ልባዊ ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

    በአዲስ አበባ፣ የካ ክፍለ ከተማ፣ ወረዳ 12፣ ልዩ ስሙ አባዶ ቁጥር 1 እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የተሠራችው የደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ  ቤተ ክርስቲያን፣ ሕገ ወጥ ግንባታ በሚል በደንብ ማስከበር ጽ/ቤቱ በከፊል የፈረሰባቸው መኾኑን የገለጹ ካህናትና ምእመናን፣ የድረሱልን ጥሪ አሰሙ፡፡
በከተማው መልሶ ማልማት ወደ አካባቢው የሔዱት ነዋሪዎቹ፣ ሥርዓተ አምልኰ የሚፈጽሙበት ቤተ ክርስቲያን ተቸግረው መቆየታቸውንና ከአራት ወራት በፊት፣ ከግለሰቦች በስጦታ ባገኙት ቤትና ቦታ ላይ በሀገረ ስብከቱ ፈቃድ በቅድስት አርሴማ ስም ቤተ ክርስቲያን ተክለውና አስባርከው በመገልገል ላይ እንደነበሩ ካህናቱና ምእመናኑ ገልጸዋል፡፡500 ካሬ ሜትር ስፋትና 30 ቆርቆሮ ቤት ያለውን ቦታ ለመኖርያና ለእርሻ ይገለገሉበት የነበሩት ግለሰቦች፣ በስማቸው ተመዝግቦ ግብር ይገብሩበት እንደነበርና ሕጋዊ ባለይዞታዎች ለመኾናቸው የሚያረጋግጥ ማስረጃ እንዳላቸው ካህናቱና ምእመናኑ ጠቅሰዋል፤ ለቤተ ክርስቲያን መሥሪያ በስጦታ ሲያበረክቱም፣ በውል ተቀባይነት የተረከቡት፣ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት የተወከሉ የመሥራች ኮሚቴው ካህናት መኾናቸውን አስረድተዋል፡፡
የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤትም፣ የነዋሪዎቹን ማመልከቻና በአባሪነት ያቀረቧቸውን ማስረጃዎች መሠረት በማድረግ፣ ቤተ ክርስቲያን ለማነጽ ይቻል ዘንድ የወረዳው አስተዳደር ጽ/ቤትና የሚመለከታቸው አካላት አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ በደብዳቤ መጠየቁን አውስተዋል፡፡
ኾኖም፥ የወረዳው አስተዳደር፣ ከኹለት ሳምንት በላይ አንዳችም ምላሽ ሳይሰጥ ቆይቷል፤ ያሉት ካህናቱና ምእመናኑ፣ ዝምታውን እንደ ይኹንታ በመቁጠር፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የታዘዘላቸውን ጽላት አስገብተው መንፈሳዊ አገልግሎት መጀመራቸውን ገልጸዋል፤ የግለሰብን ቤት በቀጥታ
ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠቀም ስለሚከብድም፣ ዲዛየኑንና ቆርቆሮውን መቀየራቸውን ጠቅሰዋል፡፡
መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን በማከናወን ላይ ሳሉም፣ የወረዳው የደንብ ማስከበር ጽ/ቤት፣ የንብረት ማስቀመጫ ኮንቴይነሩ ብቻ ሲቀር ሌላውን አፍርሶ ንብረቱን ወደ ፖሊስ ጣቢያ ማስገባቱን፣ ስምንት ካህናትም መደብደባቸውንና የመሥራች ኮሚቴው አባላትም ለአራት ቀናት ታስረው
እንደነበር ነዋሪዎቹ ተናግረዋል፡፡የታሰሩት ከተፈቱ በኋላ፣ ጉዳዩ በሕግ ታይቶ ባለመብት መኾናቸው እስኪረጋገጥ፣ ያለው ንብረት ቁልፉ ተከብሮ እንዲቀመጥ በፍርድ ቤት የእግድ
ትእዛዝ ቢያስወጡም፣ አጥሩና ምእመናኑ ለጥላ የሚገለገሉበት ሸራ፥ በደንብ ማስከበር ጽ/ቤቱ መፍረሱን፤ ዶማ፣ አካፋ፣ ድጅኖ የመሳሰሉ መሣሪያዎችም መወሰዳቸውን፤ ዘወትርም ዛቻና ማስፈራሪያ እየደረሰባቸው እንዳለ ዘርዝረዋል፡፡“ሕገ ወጥ ብንኾን፣ በሕግ እንጠየቃለን እንጂ ኢሰብአዊ በኾነ ኹኔታ ሊደበድቡንና ዘወትር እያስፈራሩን ሊቀጥሉ አይችሉም፤” ያሉት አንድ ካህን፣ መንግሥት ስለ እምነት ነጻነት ከሚናገረው አንጻር፣ “እነዚኽ ሰዎች እነማን እንደኾኑ ለመናገር እንቸገራለን፤” ሲሉ ምሬታቸውን ገልጸዋል፡፡በአኹኑ ወቅት በመቅደስነት የሚገለገሉበት፣ የንብረት ማስቀመጫ ኮንቴነር መኾኑን ጠቅሰው፣ ለአራት ወራት የተቀደሰበት ቤተ ክርስቲያን እንዳይፈርስና ተረጋግተው ማገልገል እንዲችሉ፣ ለክፍለ ከተማ አስተዳደሩ የደንብ ማስከበር ጽ/ቤት ትእዛዝ እንዲሰጥላቸው፣ ለከንቲባው ጽ/ቤት መጠየቃቸውን አመልክተዋል፤ ጉዳዩ በፍ/ቤት ለመጋቢት 27 ለውሳኔ መቀጠሩንም አስታውቀዋል፡፡   ስለጉዳዩ የደንብ ማስከበር ጽ/ቤቱን አስተያየት በስልክ ለማግኘት ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ፣ ጥሪ ባለመመለሱ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡





    አዲስ ኢንተርናሽናል ባንክ ከትናንት በስቲያ በሸራተን ሆቴል በላኪነት፣ በአስጎብኚነት፣ በማማከርና በገንዘብ አስቀማጭነት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ደንበኞቹ የሰርተፍኬትና በሦስት ደረጃ የዋንጫ ሽልማት ሰጠ፡፡
የፕላቲኒየም ተሸላሚ የሆኑት ድርጅቶች ካቤ ፒኤልሲ፣ የይርጋጨፌ የገበሬዎች ኅብረት ሥራ ማኅበራት ዩኒየን፣ ሐግቤስ ፒኤልሲና ግሪንላንድ ፒኤልሲ ሲሆኑ ሌሎችም የወርቅና የብር ዋንጫ ተሸልመዋል፡፡
አዲስ ኢንተርናሽናል ባንክ በአብዛኛው በኅብረት ስራ ማህበራት፣ እድሮች፣ አነስተኛ የብድር አቅራቢ ተቋማትና ግለሰቦች የተመሰረተ ሲሆን የባለአክሲዮኖቹም ቁጥር በቀጥታና በተዘዋዋሪ ከ300,000 በላይ ይሆናል፡፡
ባንኩ ከጊዜ ወደ ጊዜ የቅርንጫፍ ስርጭቱን በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች ለንግድ ስራ ምቹ በሆኑ ቦታዎች እያስፋፋ ሲሆን ሞባይልና ኢንተርኔት አገልግሎት ጨምሮ፤ ሁሉንም ቅርንጫፎቹን በመረጃ መረብ በማገናኘት ቀልጣፋ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑ ታውቋል፡፡



የዘንድሮ የአድዋ በዓልን አስመልክቶ ለአራተኛ ጊዜ የተካሔደው ከአዲስ አበባ አድዋ ‹‹ጉዞ አድዋ 4›› የእግር ጉዞ ከጥር 9 ጀምሮ የካቲት 23 ቀን 2009 ዓ.ም በደማቅ አቀባበል በአድዋ ከተማ መጠናቀቁ ይታወቃል፡፡ የእግር ጉዞውን በስኬት ያጠናቀቁ ተጓዦችን በደማቅ ስነስርዓት ለመቀበል
የፊታችን ሰኞ መጋቢት 11 ቀን ከምሽቱ 11፡45 ጀምሮ በአምስት ክሎ ብሔራዊ መዚየም ቅጥር ግቢ በሚገኘው ሉሲ ሬስቶራንት አዳራሽ፣ ልዩ ልዩ ኪናዊ ዝግጅቶችና የእራት ምሽት ተዘጋጅቷል፡፡
ለዘንድሮው ጉዞ አድዋ መሳካትና በሀገር አቀፍ ደረጃ የዓድዋ ክብረ በዓል ደማቅ እንዲሆን የላቀ ሚና ያበረከቱ የሚዲያ ተቋማትና ግለሰቦች የክብር አቀባበሉ ሥነስርዓት ተካፋይ ይሆናሉ ተብሏል፡፡
‹‹ጉዞ ዓድዋ›› በቀጣይ ዓመታት የአፍሪካ ተጓዦችን በእግር ጉዞው ለማሳተፍ ያለውን እቅድም በይፋ የሚገልጽበት ምሽት እንደሚሆን ይጠበቃል፡፡

 

  የቀድሞ የህፃናት አምባ ውስጥ አድገው በተለያዩ የስራ መስክ በተሠማሩ ግለሠቦች የተቋቋመው ‹‹ትምህርት ለተቸገሩ በጎ አድራጎት ማህበር›› መጋቢት 10 ቀን 2009 ዓ.ም የገቢ ማሠባሠቢያ ፕሮግራም ያካሂዳል፡፡
ከ3 መቶ በላይ የትምህርት እድል ማግኘት ያልቻሉ ህፃናትን በኮተቤ ኪዳነምህርት ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በከፈተው ትምህርት ቤት በማስተማር የሚታወቀው ማህበሩ፤ በአሁኑ ወቅት ይህን በጎ ተግባር ለማከናወን የአቅም ውስንነት ስላጋጠመው የእርዳታ ማሠባሠቢያ መርሃ ግብር ለማዘጋጀት መገደዱን አስታውቋል።
በዚህም መሰረት መጋቢት 10 ቀን 2009 ዓ.ም ከላምበረት አዲሱ መናኸሪያ ተነስቶ እስከ ኮተቤ ኪዳነ ምህረት ቤተክርስቲያን የ3.5 ኪሎ ሜትር የእግር ጉዞ በማዘጋጀትና የሙዚቃ ዝግጅትን አካቶ የገቢ ማሠባሠቢያ ሰፊ ፕሮግራም እንደሚያደርግ አስታወቆ፤ በእለቱ ድጋፍ እንዲደረግለት ጥሪ አድርጓል፡፡

 በጅማ ዩኒቨርሲቲ መምህራን ኮሌጅ የ2ኛ ዓመት የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተማሪ፣ የሆነው ወጣት በአንገት ማዕተብ ጉዳይ ከመምህሩ ጋር ተጋጭቶ “የትምህርት ውጤቴ ተበላሸ” በሚል ራሱን አጠፋ፡፡
ተስፋዬ ገመዳ የተባለው ተማሪ የስነ ልቦና ሳይንስ መምህሩ በቡድን ያዘዙትን አሳይመንት ስራ አዘጋጅቶ በመድረክ ላይ ሊያቀርብ ሲል መምህሩ፣ “በአንገትህ ላይ ያደረከውን ማተብ ወይ አውልቅ ወይም ሸፍነው” ሲሉት ተማሪው፤ “ይህ የእምነቴ መገለጫ ነው፤ ያዘዙኝን ማድረግ አልችልም” የሚል ምላሽ እንደሰጣቸውና መምህሩም “ያዘዝኩህን ማድረግ ካልቻልክ የሰራኸውን ማቅረብ አትችልም” በማለታቸው ስራውን ሳያቀርብ መቅረቱንና ከመድረኩ ወርዶ በእጁ የያዘውን የቡድን  ስራ ሪፖርት በንዴት ቀዳዶ መቀመጡን የአይን እማኞች አስታውሰዋል፡፡ በወቅቱ ተማሪው ክፍለ ጊዜውን አቋርጦ ከክፍሉ መውጣቱንና ተመልሶ  ሊገባ ሲል መምህሩ አትገባም ብለው እንደከለከሉትና፣ ተማሪውም ስሜታዊ ሆኖ ከመምህሩ ጋር ለፀብ መጋበዙን፣ ተማሪዎችም በመሃል ገብተው እንደገላገሏቸውና የአካዳሚክ ዲኑ በቦታው ተገኝተው ስለተፈጠረው ችግር ተማሪዎችን በመጠየቅ፣ ፀቡን ማረጋጋታቸውን ተማሪዎች ለአዲስ አድማስ ጠቁመዋል፡፡
በሌላ ቀን እንደተለመደው ተማሪው የስነልቦና ክፍለ ጊዜ ትምህርቱን ለመከታተል ወደ ክፍል ሲገባ መምህሩ በድጋሚ ከክፍል እንዳስወጡት፣ ተማሪውም ለአካዳሚክ ዲኑ አቤቱታ ማቅረቡንና ዲኑም የትምህርቱ የመጨረሻ ክፍል ጊዜ ስለሆነ ‹‹በቃ ተወው በውጤትህ ላይ ምንም ለውጥ አያመጣም›› ብለው አረጋግተው እንደሸኙት፣ የተማሪው የቅርብ ጓደኞች ገልፀዋል፡፡
በኋላም ፈተና እንዲወስድ የተፈቀደለት ሲሆን የተለጠፈውን የፈተና ውጤት ሲመለከት ግን “No Grade” (ምንም ውጤት የለም) የሚል ስለነበር ወዲያው በንዴት ወደ ተከራየበት ቤት በማምራት የዚያኑ እለት ራሱን ግቢ ውስጥ ባለ የማንጎ ዛፍ ላይ  ሰቅሎ ማጥፋቱን የቅርብ ጓደኞቹ ገልፀዋል፡፡
ፖሊስና የአካባቢው ህብረተሰብ በቦታው ደርሶ ከተሰቀለበት ሲያወርዱት ነፍሡ ከስጋው  እንዳልተላቀቀችና ወደ ሆስፒታል በመሄድ ላይ ሣለ ህይወቱ ማለፉን የጠቆሙት ምንጮች፤ የቀብር ሥነስርዓቱም ከትናንት በስቲያ በትውልድ አካባቢው በሰሜን ምዕራብ ሸዋ፣ ደገሞ ወረዳ መፈፀሙን ለማወቅ ተችሏል፡፡
አስከሬኑን ለቤተሰብ ያደረሱት መርማሪ ፖሊስ ዮሐንስ መገርሳ፤ ተማሪው ከመምህሩ ጋር በመጣላቱ ራሱን  እንዳጠፋ ጥርጣሬ መኖሩንና የሆስፒታል የምርመራ ውጤት በማስረጃነት እየተጠበቀ መሆኑን ጠቁመው፣ ጉዳዩ ገና በመጣራት ላይ ነው ብለዋል - ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፡፡

 ከቻይና ስመ-ጥር የጫማ አምራች ኩባንያዎች አንዱ የሆነውና ከአምስት አመታት በፊት በኢትዮጵያ ፋብሪካውን ከፍቶ የማምረት ስራ የጀመረው ሁጂያን ግሩፕ፤ ኢንቨስትመንቱን ለማስፋፋትና ለ100 ሺ ሰዎች ተጨማሪ የስራ ዕድል ለመፍጠር ማቀዱን አስታወቀ፡፡
ሁጂያን ግሩፕ ለ6 ሺህ ያህል ኢትዮጵያውያን ዜጎች የስራ ዕድል መፍጠሩንና ለአገሪቱ የውጭ ምንዛሬ በማስገኘት ረገድ አስተዋጽኦ ማበርከቱን ያስታወሱት የኩባንያው ፕሬዚዳንት ዣንግ ሁዋሮንግ፤ 100 ሺህ ያህል አዳዲስ የስራ ዕድሎችን የመፍጠርና ካፒታሉን ወደ 10 ቢሊዮን ዶላር የማሳደግ ዕቅድ እንዳለው መግለጻቸውን ፒፕልስ ዴይሊ ድረገጽ ዘግቧል፡፡
ኩባንያው በኢትዮጵያ በከፈተው ፋብሪካ እያመረተ ለውጭ ለገበያ የሚያቀርባቸው የጫማ ምርቶች፣ የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ልጅ የሆነቺው ኢቫንካ ትራምፕ ያቋቋመቺውን ኢፖኒመስ የተባለ ኩባንያ ጨምሮ በበርካታ የአውሮፓ አገራት ኩባንያዎች ዘንድ ተወዳጅነት ማትረፋቸውንም ፕሬዚዳንቱ ተናግረዋል፡፡

 ጥልቅ ሀዘን እንደተሰማቸው ለፍ/ቤቱ ተናግረዋል
                                      
       ህገ መንግስታዊ ስርአቱን በኃይል ለማስወገድ ሙከራ አድርገዋል እንዲሁም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ድንጋጌዎች ተላልፈዋል በሚልና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ክስ የተመሰረተባቸው ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ ለፍ/ቤት ያቀረቡት የዋስትና ጥያቄ ተቀባይነት አላገኘም፡፡
አንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር መረራ ጉዲና የካቲት 24 ቀን 2009 ዓ.ም በነበራቸው ቀጠሮ፣ የተከሰሱት በወንጀል ህጉ ስለሆነና ተከሳሹ ከዚህ ቀደም የነበራቸው የፖለቲካ ታሪክ፣ ከቤልጂየም ሲመለሱ እንደሚታሰሩ እየተነገራቸው እንደመጡና ከሀገር የመኮብለል ፍላጎት የሌላቸው መሆኑ ታይቶ እንዲሁም የስኳር ህመምተኛ በመሆናቸው በዋስትና ሆነው ጉዳያቸውን እንዲከታተሉ እንዲፈቀድላቸው ጠይቀው እንደነበር ይታወሳል፡፡
አቃቤ ህግም የተጠረጠሩበት ወንጀል ህገ መንግስታዊ ስርአቱን በኃይል የመናድ ሙከራ በመሆኑ በዋስትና ቢወጡ መረጃ ሊያሸሹ ይችላሉ በሚል የዋስትና ጥያቄው ውድቅ እንዲደረግለት ጠይቋል፡፡
የግራ ቀኙን አስተያየት የመረመረው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት፤ ተጠርጣሪው በተከሰሱበት የህግ አንቀፅ ጥፋተኛ ሆነው ከተገኙ ከ15 ዓመት በላይ ወይም በእድሜ ልክ አሊያም በሞት ሊያስቀጣ የሚችል በመሆኑ ዋስትናውን ሳይቀበለው ቀርቷል፡፡
በችሎቱ ማጠናቀቂያ ላይ ዶ/ር መረራ የምናገረው አለኝ ብለው ሲፈቀድላቸው፡-
“ከእነ ጀነራል መንግስቱ ነዋይና ጀነራል ታደሰ ብሩ ዘመን ጀምሮ ከአንድ ትውልድ በላይ ገዳዮችና ሟቾች፣ ታሳሪዎችና አሳሪዎች በበዙበት የሀገራችን የፖለቲካ ድራማ ውስጥ በመቆየት አንድ ከሆዱ በላይ ለሀገሩ የሚያስብ ምሁር ማድረግ እንዳለበት ሁሉ፣ ከአርባ አምስት አመታት በላይ ለሀገሩ የተሻለ ለውጥ እንዲመጣ በታማኝነት መታገሌ እየታወቀ ወደ ጎን መገፋቴን፤ ለሁላችንም የምትሆንና በእኩልነት የምታስተናግደን ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያ እንድትፈጠርና ነፃ የፍትህ ስርአት በሀገራችን እንዲሰፍን ላለፉት 25 ዓመታት በመታገሌ መከሰሴ አንሶ የሀገሪቱ ፓርላማ አባል ጭምር የነበርኩት ሰው፣ ለተራ ወንጀለኛ የሚፈቀድ የዋስ መብት በመከልከሌ የተሰማኝን ጥልቅ ሀዘን ለራሴ ብቻ ሳይሆን እኛም ሆንን ልጆቻችን በሰላም ይኖሩበታል በምንለው መከረኛ ሀገራችንና አላልፍለት ብሎ ለታመሰው ለመላው መከረኛ ህዝባችን ጭምር መሆኑ እንዲታወቅልኝ ነው” የሚል ንግግር አድርገዋል፡፡

Saturday, 11 March 2017 12:53

መጫወቻ ፍለጋ

የሠፈር ልጆች ቅዳሜ-ቅዳሜ መጫወቻ ፍለጋ ዙረት እንሔድ ነበር፡፡ ብዙውን ጊዜ ምርጫችን ፈረንጆች ቤት ጓሮ ማንጎዳጎድ ነበር፡፡ ፈረንጆቹ ከቤታቸው አጥር ግቢ ውጪ ጉድጓድ ቆፍረው ቆሻሻውን እዚያ ይጥሉታል፡፡ ዘበኞቻቸውም ጠቃሚ የሆነውን ዕቃ ይቃርማሉ፡፡ በተቀረው ላይ እሳት ለኩሰው ይለቁበታል፡፡ አንዳንዴ ከመቃጠሉ በፊት ደርሰን ደጋግ ዘበኞች ካጋጠመን ደስ ያለንን ዕቃ እንወስዳለን፡፡ ግን ብዙውን ጊዜ የሚያጋጥሙን እርጉም ዘበኞች ስለነበሩ ያባርሩናል፡፡ ሸሽተን ከሌላ ቪላ ቤት ጓሮ ፍለጋችንን እናጧጡፋለን፡፡
ከዕለታቱ በአንዱ ቀን ብትንትኗ የወጣ አሻንጉሊት አገኘን፡፡ ቀጢሳው ከትከሻዋ እስከ ዳሌዋ ያለው የአሻንጉሊቷን አካል ሲያገኝ “ባትጋሩኝ! በትኩስ እንጀራ በመርፌ ቀዳዳ!” ብሎ ጮኸ፡፡
አሻንጉሊቷ ጭንቅላት፣ እጅና እግር እንደሌላት ካስተዋለ በኋላ “በእናታችሁ ልጆች! የተቀረውን አካሏን ካገኛችሁት ትሰጡኛላችሁ? የአሻንጉሊቷ ሙሉ አካል ከተገኘ ልብስ ሰፍተንላት ሁላችንም እንጫወትባታለን፡፡” አለ ቀጢሳው እየተለማመጠን።
ብዙም ሳይቆይ ኃይሉ ዶሮ “ባትጌ!” አለና ጮኸ። የአሻንጉሊትዋን እጆች ሽቅብ እንደ ዋንጫ ሰቅሎ እያሳየን፡፡
“ለቀጢሳው ስጠው!” እያልን ሁላችንም ለመነው፡፡ ሰጠው፡፡
“ዶሮ ደግ ልጅ ነው” አልን ሁላችንም፣ ቆሻሻውን ማገለባበጡን እየቀጠልን፡፡
የቆሻሻው ትንፋግ አይነሳ! አዋቂን ሰው ከአገር ያስለቅቃል፡፡ እኛ ግን መጫወቻው በልጦብን ያንን ክርፋት የልጅነት አፍንጫችን ችሎታል፡፡
ከጥቅም ውጭ የሆኑ የሕክምና ዕቃዎች፣ የምግብ ማሸጊያ ፓኮዎች፣ ቆርቆሮዎች፣ አርተፊሻል ፀጉር፣ የፀጉር ማስያዣ፣ ካርቶኖች፣ ፊኛዎች አገኘን። ፊኛውን እየተቀባበልን ነፋነውና ተጫወትንበት፡፡ (በበኋለኛው የሕይወት ዘመኔ ፊኛ እያልን ስንነፋው የነበረው ኮንዶም እንደነበረ ተገንዝቤያለሁ፡፡)
እዚያው ትንፋጉ ላይ ሆነን አስቂኝ ትዕይንት እየሰራን ያንን መራር ሕይወት እናጣፍጠው ነበር፡፡ ቀጢሳው ግማሽ ጎኑ የተቃጠለውን አርተፊሻል ፀጉር አናቱ ላይ አድርጎ፣ የተሰበረ የፀጉር ጌጥ ሰክቶበት እንደ ፈረንጅ ኮረዳ እየተሽኮረመመ “ዊስ ዋይስ” ብሎ በራሱ እንግሊዝኛ ተናገረ፡፡
ጎቢጥ ያንን አንድ ዓይኑ ላይ መስታወት የሌለውን መነፅሩን አደረገና አፉ ላይ የሲጋራ ቁራጭ ወትፎ እንደ ፈረንጅ ጎረምሳ ጎርነን ባለ ድምፅ፤ “ዋት ኢዝ ዊስ ዋይ?” አለ በብረት ዘንግ ቆሻሻውን እየቆፈረ፡፡ የአሻንጉሊትዋን እግሮች አገኘ፡፡ ለቀጢሳው ሰጠው።
ቀጢሳው ቻርሊ ቻፕሊን ፊልም ላይ ባየነው ስልት በደስታ ተውረግርጎ ሹል አፉን አሞጠሞጠና ሲሳይ ጎቢጥን ሳመው፡፡
ፍለጋችን ቀጠለ፡፡ ውሮ አንድ ነገር ደብቆን ኪሱ ሲከት ሴምላል አየውና፤ “ምን አገኘህ?” ሲል ጠየቀው፡፡ ሁላችንም ካቀረቀርንበት ቀና አልን፡፡ ውሮ ቁንጮውን እያከከ “ምንም አላገኘሁም!” አለ፣ ኪሱን ጨብጦ ላለማስፈተሽ እየሞከረ፡፡
“እስኪ እናቴ ትሙት በልና ማል?!” ሲል ሴምላል ንፍጡን ሽቅብ እየሳበ ጠየቀው፡፡ ውሮ መማሉን ፈራ፡፡ በዚህ ምልልስ ወቅት መኩዬ ቀጫጫው እንደ እባብ ተስባ ከውሮ ኋላ ደርሳ ከኪሱ በፍጥነት አንድ ነገር ስትስብ የአሻንጉሊቷ ጭንቅላት መሬት ዱብ አለ፡፡
“ወይኔ አሻንጉሊቴን!” ሲል ውሮ ጩኸቱን አቀለጠው፡፡ መኩዬ ቀጫጫው የአሻንጉሊት ጭንቅላት ከመሬት አንስታ እየደባበሰች ለቀጢሳው እንዲሰጠው ለመነችው፡፡
ውሮ “እምቢ” አለ፡፡
ሁላችንም ብንለምነው ችክ አለ፡፡ እርሱም የራሱ አሻንጉሊት እንዲኖረው፣ የተቀረውን አካል በሽቦና በጨርቅ ሠርቶ ሊጫወትበት መፈለጉን በልቅሶ ዜማ አወራን፡፡ በዚህ ራስ ወዳድነቱ ሁላችንም አኮረፍነው፡፡ መኩዬ ቀጫጫውም የአሻንጉሊቷን ጭንቅላት አፍንጫው ላይ ወረወረችለት፡፡
(“ልጅነት” ከተሰኘው የደራሲ ዘነበ ወላ
መፅሀፍ ላይ የተቀነጨበ)

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ - ዓይነ - ሥውር እናት የነበረችው አንድ ልጅ ነበረ፡፡ ይሄ ልጅ እናቱን አደባባይ ማውጣት አይፈልግም፡፡ ያፍርባታል፡፡ በሄደበት ቦታ ሁሉ ሌሎች ልጆች ስለ እናታቸው ሲያወሩ፣ እሱ አያወራም፡፡ ሌላው ቀርቶ ሌሎቹ ስለ እናታቸው ደግነት ሲያወሩ እሱ እናቱን አያነሳም። እናቱ በእናትነቷ እስክትሸማቀቅና እስክትሸሸግ ድረስ በሰፈር ልጆች መሳቂያ መሳለቂያ እንድትሆን አደረጋት፡፡
በትምህርቱ እየገፋ ታዋቂ ልጅ እየሆነ ሲሄድ፣ ስለ እናቱ መናገሩን ጨርሶ ተወ - ያለ እናት የተወለደ እስኪመስል ድረስ፡፡ ውጪ አገር ሄዶ አድጎ ተመንድጎ፣ አንቱ ተብሎ ትልቅ ስራ ያዘ፡፡ እናቱን ረሳት፡፡ እናቱን የከዳና የናቀ መሆኑን ግን የሚያውቅ ማንም የለም፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ትውልድ አገሩ ውስጥ ለሚደረግ ትልቅ ኮንፈረንስ ተጋበዘና ወደ ሀገሩ መጣ፡፡
ስብሰባው ሲያበቃ እስከ ዛሬ ረስቷት የነበረችውን እናቱን እስቲ ከመጣሁ አይቀር ልያት ብሎ ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ቤት ግን የጠበቀችው እናቱ ሳትሆን፣ የእናቱ ታናሽ እህት፣ አክስቱ ናት፡፡
“እናቴስ ወዴት አለች?” አለና ጠየቀ እንደደረሰ፡፡
አክስቱም፤ “እናትህ የለችም?”
ልጅ፤ “ወዴት ሄደች?”
አክስት፣ “ወደማይቀረው አለም”
ልጁ ያልጠበቀው ነበረና ድንጋጤ ላይ ወደቀ፡፡ አለቀሰ፡፡
ሲረጋጋ፤ “እናትህ ከመሞቷ በፊት ‹ድንገት ልጄ ከመጣ ይሄን ደብዳቤ ስጪልኝ› ብላለች፡፡ እንካ ውሰደው” ብላ አክስቱ ትሰጠዋለች፡፡
ሲፈራ ሲቸር እጁ እየተንቀጠቀጠ ይቀበላትና ደብዳቤውን ከፍቶ ያነበዋል፡፡ እንዲህ ይላል፡-
“ልጄ! አንድ ልጄ ሆይ!
ብትገፋኝም፣ ብትርቀኝም፣ ብትንቀኝም ብታስንቀኝም፣ ብትጠላኝም፣ ብታስጠላኝም፣ ብታኮርፈኝም፣ ሰዎች እንዲያፍሩብኝ ብታደርግም፣ አሁንም ያው አንድ ልጄ ነህ! ህይወቴ ከማለፉ በፊት አንድ ነገር ልነግርህ እፈልጋለሁ፡-
ወጣት ሆነህ አንድ ዐይንህን ክፉኛ ያምህ ነበር፡፡ ሐኪም ቤት ወስጄህ ዶክተሩ ዐይንህ ሊጠፋ እንደሚችልና በቀዶ - ጥገና ሌላ ዐይን ካልተተከለልህ ተስፋ እንደማይኖርህ፣ ጨርሶም እንደሚጠፋ፣ ነገረኝ፡፡ የአንተ፣ የነገ ተስፋዬ፣ ገና ብዙ ማየት ያለብህ አንድ ልጄ፤ ዐይንህ - ብርሃንህ ከሚጠፋ የእኔ ዐይን ይጥፋ፤ ብዬ፣ የእኔ ዐይን ይጥፋና አንተ ብርሃን ይኑርህ ብዬ፣ ዐይኖቼን አስወልቄ ላንተ አስተከልኩልህ!! ዛሬ አንተ ሁለት ዐይን የኖረህና እኔ ዐይነ - ስውር የሆንኩት ለዚህ ነው! እይበት! ሰው ሁንበት ብዬ ነው!”
ልጅ በእጁ ይዞ የቀረው ፀፀትን ብቻ ነው!
*   *   *
እናትየውን ኢትዮጵያን አድርገን ብናይ ብዙ ነገር እንማራለን! የዛሬው ትውልድ ከላይ እንደተጠቀሰው ወጣት እንዳይሆን እንመኛለን፡፡
ዛሬም ወጣቱ የማያፍርበት አገር እንዳለው ልናሳውቀው ይገባል፡፡ ከራስ ወዳድነት የፀዳች አገር እንዳለችው በኩራት ማሰብ ይገባዋል፡፡ ጽጌረዳ ያለ እሾክ እንደማትኖር ልብ ይል ዘንድ ልንመክረው ይገባል!
ድርቅ እና የኑሮ ውድነት ዛሬም ከጫንቃችን ላይ አልወረዱም! “የደመናው ሎሌ” የሚለውን ግጥም ያስታውሰናል፡-
ለወትሮው ደመና ፊቱ እየጠቆረ
ዐይኖቹን አሻሽቶ ያነባ ነበረ
    ይዘንብ ነበረ
የዘንድሮ ሰማይ ፈጋግ ሰማያዊ
መልኩን አሳምሮ
ስንቱን ፈጀ በላ ከራብ ተመሳጥሮ
የምድር ከርስ አረረ
አገር ጦም አደረ
ሰው ምጡ ጠናና
ዐይኖቹን አቀና
እንዲሁ ከርተት ከርተት ሰማይ ለሰማይ
ውሃ የለሽ ህዋ ጠብታ-አልባ ጠፈር
ሰማይ አይታረስ በዐይን ብሌን ሞፈር
የዳመናው ሎሌ የዳመናው አሽከር
የዕለት ግብሩ ሆነ ጦም ውሎ ጦም ማደር
ዕንባውን እረጫት ሽቅብ ወደ ላይ ድንገት
ዝናብ ሆና ትወርድ ይሆን ወይ?!
ታህሣሥ 1977 ዓ.ም
(ለ1977 ድርቅ)
የመንግስት ሠራተኞች የተጨመረውን ደሞዝ መሰረት ያደረገ የነጋዴዎች የሸቀጥ ዕቃ ዋጋ መጨመር፤ ሌባና-ፖሊስ ጨዋታ አስገራሚ ነው! ህዝብና ነጋዴ አይጥና ድመት ሆነው መኖር የለባቸውም! ውስጠ-ነገሩ የሀገራችንን ነገር፣ የሀገራችንን የፖለቲካ ሂደት፣ የየትውልዱን ማንነትና የፖለቲካ ተዋንያን ከእናት አገራቸው ጋር ያላቸውን ትሥሥር ሊያመላክተን የሚችል ነው፡፡ መልካም-ትውልድ የመሠረቱን አይረሳም፡፡ ሰፊውን የሀገሩን ሥዕል በሆደ ሰፊነት ያስተውላል፡፡ ከሀገር በፊት የሚመጣን ራስ ተኮርና ራስ ጠቀም አካሄድ ያስወግዳል፡፡ ከእርስ በእርስ መናቆርና መወጋገዝ፤ ከእኩይ ሙግት፣ ከእኔ ልግዘፍ ፖለቲካ፣ ከቀረርቶና ከሜዳሊያ ፍለጋ ሩጫ ራሱን ያገልላል ‹‹ከወጡ ሳይወጠወጥ ወስከንባዩ ፍጥጥ›› ጨዋታ ራሱን በጊዜ ይገላግላል!
መጪው ትውልድ አርአያ ይሻል! አርአያ ልንሆነው ልባችን ይሙላ፣ ሁሉን ነገር ለመንግስት ጥለን አንችለውም! መንግሥት ያለውን ቢል ህዝብ እንደምን ተቀበለው ብሎ ጥናት ማካሄድ የነገራችን ሁሉ አልፋ- ኦሜጋ ነው፡፡ መንግሥት ሊሣሣት ይችላል፡፡ ማረሚያ ነጥቦቹ (Check-points) እኛ ነን!
ተሳስተሃል አቅጣጫህን ቀይር ማለት ኃላፊነታችን ነው (We are the watch-dogs) ይላሉ ፈረንጆቹ እንጂ ተረቱ እንደሚለው፤ ‹‹ንጉሥ የቆረጠው እጅ እንዳለ ይቆጠራል›› እያልን ብዙ አንራመድም! በቀናነት ዕድሜውን ይስጠን!!