Administrator

Administrator

            ሸፍተው የነበሩ የዞኑ የፖሊስ ልዩ ሃይል አዛዥና የሚሊሽያ አባላት እጃቸውን ሰጡ

        በጋምቤላ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በጎደሬ ወረዳ፣ በመዠንገር ዞን በተቀሰቀሰውና አሁንም ድረስ በአንዳንድ ቦታዎች በቀጠለው ግጭት እጃቸው እንዳለበት የተጠረጠሩ የክልሉ ባለስልጣናት ያለመከሰስ መብታቸው ተነስቶ በቁጥጥር ስር እየዋሉ ነው፡፡ በአዲስ አመት ዋዜማ የተቀሰቀሰውና ከ40 በላይ ሰዎችን ህይወት የቀጠፈው ግጭት መነሻ ከመሬት ባለቤትነት ጋር የተያያዘ እንደሆነ ለአዲስ አድማስ የገለፁት ምንጮች፤ “ደገኞች መሬታችንን ይልቀቁ” የሚሉ የአካባቢው ተወላጆችና አንዳንድ የክልሉ ባለስልጣናት በመንግስት ተግባራዊ እየተደረገ ያለውን የሰፈራ ፕሮግራም ተገን በማድረግ ነባር ይዞታ ያላቸውን ነዋሪዎች በማፈናቀላቸው ግጭቱ መፈጠሩን ተናግረዋል፡፡

በአካባቢው ተወላጆችና ከሌሎች አካባቢዎች በመጡ ነዋሪዎች መካከል ለረጅም ጊዜ የቆየና በየጊዜው የሚያገረሽ ግጭት እንዳለ የሚታወቅ ሲሆን፣ በቅርቡ የተከሰተው ግጭት ሊቀሰቀስ እንደሚችል የፌደራል መንግስት በደረሰው መረጃ መሰረት፣ በአፈ ጉባኤ ካሳ ተክለብርሀን የተመራ ቡድን ከክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት ጋር በመተባበር በአካባቢው የማረጋጋት ስራ ቢሰራም፣ በዞኑ ያሉ አንዳንድ የፖሊስና የሚሊሺያ አባላት “መሬታችንን ይልቀቁ” የሚለው ሃሳብ እንዲሰርፅ በማድረጋቸው ግጭቱ እንደተፈጠረ ምንጮቻችን ጠቁመዋል፡፡

ግጭቱ ከተፈጠረ በኋላም የዞኑን የፖሊስ ልዩ ሀይል አዛዥ ጨምሮ የፖሊስና የሚሊሽያ አባላት ሸፍተው ጫካ መግባታቸውን የተናገሩት ምንጮች፤ በአሁኑ ወቅት አዛዡና ሌሎች ጥቂት አባላት እጃቸውን ለመንግስት ሃይሎች እንደሰጡ ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የተከሰተው ግጭት ሁነኛ መፍትሔ ካልተበጀለት፣ በአቅራቢያ ወደሚገኙ ሌሎች አካባቢዎች ሊዛመት ይችላል የሚል ከፍተኛ ስጋት መፈጠሩን ያመለከቱት ምንጮቹ፤ ከወራት በፊት ማንነታቸው ያልታወቀ የታጠቁ ሰዎች ዲማ ተብሎ በሚጠራው የክልሉ አካባቢ አስር ሰላማዊ ዜጎችን ገድለው መሰወራቸውን ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው የተከሰተው ግጭት ከክልሉ የፀጥታ ሃይሎች ቁጥጥር በላይ በመሆኑ፣ የፌደራል ፖሊስና የመከላከያ ሃይል ጣልቃ ገብቶ የማረጋጋት ስራ እየሰራ እንደሚገኝ ለማወቅ ተችሏል፡፡

                       በፊልም ባለሙያው ቴዎድሮስ ተሾመና በደራሲ አትንኩት ሙሉጌታ መካከል በተመሰረተው የመብት ይገባኛል ፍትሃብሄር ክርክር፣ ፍ/ቤት በአርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ ላይ የ10 ሚሊዮን ብር እግድ ከትናንት በስቲያ አስተላለፈ፡፡ ከሳሽ ደራሲ አትንኩት ሙሉጌታ፤ ነሐሴ 13 ቀን 2006 ዓ.ም ለፍ/ቤት ባቀረቡት ክስ፤ አርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ ለእይታ ያበቃው “ሦስት ማዕዘን” የተሰኘ ፊልም ጻሪክ በ2000 ዓ.ም ካሳተሙት “ፍቅር ሲበቀል” የተሰኘ የረዥም ልቦለድ መፅሃፍ የተወሰደ ነው የሚል አቤቱታ አሰምተዋል፡፡ “ሦስት ማዕዘን” የተሰኘው ፊልም መፅሃፋቸው ታትሞ ከወጣ ከ5 ዓመት በኋላ ለዕይታ እንደበቃ በክሳቸው የጠቆሙት ከሳሽ፤ አርቲስት ቴዎድሮስ ያለደራሲው ፈቃድ የቦታና ገፀ-ባህርያት ስሞችን በመቀያየር ብቻ የመፅሀፉን መሰረታዊ ጭብጥና የታሪክ ፍሰት በፊልሙ ውስጥ መጠቀሙን አመልክተዋል፡፡ አርቲስት ቴዎድሮስ ፊልሙን በተደጋጋሚ ለተመልካች በማሳየት ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘቱን በክስ ማመልከቻው ላይ የጠቆሙት ደራሲው፤ ተከሳሽ በፈፀሙት ተግባር ከፍተኛ የሞራል ውድቀት እንደደረሰባቸውና ፊልሙ የመፅሃፉ ቀጣይ ህትመት ላይ ተፅዕኖ እንደፈጠረ በመጠቆም የ10 ሚሊዮን ብር ካሳ ጠይቀዋል፡፡

ከሳሽ የመፅሃፉን ጭብጥ፣ መቼትና የተለያዩ ታሪኮች ከ“ሶስት መአዘን” ፊልም ታሪክ ጋር በማመሳከር ለፍ/ቤቱ በማስረጃነት አቅርበዋል፡፡ ጉዳዩን እየመረመረ የሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ ባለፈው መስከረም 6 በዋለው ችሎት፤ የክስ ማመልከቻው ለተከሳሽ ደርሶ መልስ እንዲሰጥበትና የከሳሽ ምስክሮች እንዲቀርቡ ለጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ በተጨማሪም ከሳሽ ጳጉሜ 3 ቀን 2006 ዓ.ም በፃፉት ማመልከቻ የ10 ሚሊዮን ብር ክስ ማቅረባቸውንና ቢፈረድላቸው ፍርዱን የሚያስፈፅሙበት ንብረት እንደማያገኙ በመጥቀስ ተከሳሹ በተለያዩ ባንኮች ካላቸው ገንዘብ ላይ 10 ሚሊዮን ብር እንዲታገድላቸው ማመልከታቸውን ያስታወሰው ፍ/ቤቱ፤ አቶ ቴዎድሮስ ተሾመ በዘመን ባንክ ከሚገኘው የሂሳብ ደብተራቸው 10 ሚሊዮን ብር እስከ ቀጣዩ ቀጠሮ ድረስ ታግዶ እንዲቆይ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡ አርቲስት ቴዎድሮስ ፊልሙን በተደጋጋሚ ለተመልካች በማሳየት ከ20 ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ማግኘቱን በክስ ማመልከቻው ላይ የጠቆሙት ደራሲው፤ ተከሳሽ በፈፀሙት ተግባር ከፍተኛ የሞራል ውድቀት እንደደረሰባቸውና ፊልሙ የመፅሃፉ ቀጣይ ህትመት ላይ ተፅዕኖ እንደፈጠረ በመጠቆም የ10 ሚሊዮን ብር ካሳ ጠይቀዋል፡፡

ከሳሽ የመፅሃፉን ጭብጥ፣ መቼትና የተለያዩ ታሪኮች ከ“ሶስት መአዘን” ፊልም ታሪክ ጋር በማመሳከር ለፍ/ቤቱ በማስረጃነት አቅርበዋል፡፡ ጉዳዩን እየመረመረ የሚገኘው የፌደራሉ ከፍተኛ ፍ/ቤት ልደታ ምድብ ባለፈው መስከረም 6 በዋለው ችሎት፤ የክስ ማመልከቻው ለተከሳሽ ደርሶ መልስ እንዲሰጥበትና የከሳሽ ምስክሮች እንዲቀርቡ ለጥቅምት 28 ቀን 2007 ዓ.ም ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ በተጨማሪም ከሳሽ ጳጉሜ 3 ቀን 2006 ዓ.ም በፃፉት ማመልከቻ የ10 ሚሊዮን ብር ክስ ማቅረባቸውንና ቢፈረድላቸው ፍርዱን የሚያስፈፅሙበት ንብረት እንደማያገኙ በመጥቀስ ተከሳሹ በተለያዩ ባንኮች ካላቸው ገንዘብ ላይ 10 ሚሊዮን ብር እንዲታገድላቸው ማመልከታቸውን ያስታወሰው ፍ/ቤቱ፤ አቶ ቴዎድሮስ ተሾመ በዘመን ባንክ ከሚገኘው የሂሳብ ደብተራቸው 10 ሚሊዮን ብር እስከ ቀጣዩ ቀጠሮ ድረስ ታግዶ እንዲቆይ ትዕዛዝ አስተላልፏል፡፡

   የሪያድ ልዩ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የሽብር ተግባራትን ለመፈጸም ተንቀሳቅሰዋል በሚል ክስ በተመሰረተባቸው አራት የሳኡዲ አረቢያ ዜጎችና በአንድ ኢትዮጵያዊ ላይ ከአንድ እስከ አምስት አመት የሚደርስ የእስራት ቅጣት መጣሉን አረብ ኒውስ ዘገበ ፡፡ ስሙ ያልተገለጸው ኢትዮጵያዊና አራቱ ግብረ አበሮቹ፣ የቅዱስ ቁርአንን አስተምሮት በሚጥስ መልኩ ከሚንቀሳቀሱ የአገሪቱ ጽንፈኛ ሃይሎች ጋር ግንኙነት በመፍጠር ብጥብጥ ለማስነሳት ሞክረዋል፤ ሌሎችንም ለአመጽ አነሳስተዋል በሚል በቀረበባቸው ክስ፣ ጥፋተኛ ሆነው በመገኘታቸው፣ ኢትዮጵያዊው የአምስት አመት እስራት ተፈርዶበታል፡፡ የእስር ጊዜውን ጨርሶ ከወጣ በኋላ ወደ አገሩ እንዲመለስ የተፈረደበት ኢትዮጵያዊው፣ ለሃጂና ኡምራ ጸሎት ካልሆነ በቀር፣ ከአሁን በኋላ ወደ አገሪቱ እንዳይገባም ተከልክሏል፡፡

ሁለቱ ግብረ አበሮቹ የአንድ አመት ከስድስት ወራት እስራትና ለሶስት አመታት የሚቆይ የጉዞ ገደብ የተጣለባቸው ሲሆን፣ ቀሪዎቹ ሁለቱ የአንድ አመት እስራትና ለሶስት አመታት የሚቆይ የጉዞ ገደብ ተጥሎባቸዋል፡፡ተከሳሾቹ በ30 ቀናት ውስጥ ይግባኝ ማለት እንደሚችሉ ፍርድ ቤቱ አስታውቋል፡፡ በተከሳሾቹ ላይ የተላለፈው ውሳኔ፣ ባለፉት ወራት ከተላለፉት መሰል ውሳኔዎች ጋር ሲነጻጸር ቀላል የሚባል መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ ፍርድ ቤቱ በቅርቡ ከ10 በላይ በሆኑ ተጠርጣሪዎች ላይ እስከ እድሜ ልክ የሚደርስ ቅጣት መጣሉን አስታውሷል፡፡

        በአንጋፋው ደራሲ አዳም ረታ የተጻፈው “መረቅ” የተሰኘ የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ይውላል፡፡ ለደራሲው ስምንተኛው የሆነው ይሄው መፅሃፍ፤ ከስድስት መቶ በላይ ገጾች ያሉት ሲሆን፣ በቅርቡ በተለያዩ መጽሃፍት መደብሮችና አዟሪዎች ለገበያ እንደሚውል ታውቋል፡፡ ደራሲ አዳም ረታ ከዚህ በፊት “ማህሌት”፣ “ግራጫ ቃጭሎች”፣ “እቴሜቴ ሎሚ ሽታ”፣ “አለንጋ እና ምስር”፣ “ከሰማይ የወረደ ፍርፍር”፣ “ህማማት እና በገና” እና “ይወስዳል መንገድ፣ ያመጣል መንገድ” የተሰኙ ተወዳጅ የአጫጭርና የረጅም ልቦለድ መጽሃፍትን ለንባብ አብቅቷል፡፡ አዳም ከዚህ በተጨማሪም፣ በአይነቱ ለየት ያለና ከ1ሺህ 600 በላይ ገጾች እንደሚኖረው የተነገረለትን፣ “የስንብት ቀለማት” የተሰኘ ረጅም ልቦለዱን እያጠናቀቀ እንደሚገኝ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡ለረጅም አመታት ኑሮውን በባህር ማዶ ያደረገው አዳም ረታ፣ ሰሞኑን ወደ አዲስ አበባ እንደመጣ ለማወቅ ተችሏል፡፡

Saturday, 13 September 2014 15:54

ሳቅ አታ‘ቅም

ሳቅ አታ‘ቅም
“ሳቅ አታ‘ቅም አሉኝ - ሳቅ እንዳስተማሩኝ
ሳላ‘ቅ ብስቅ እንኳን - ከሳቅ ላይቆጥሩልኝ
እንዴት ብዬ ልሳቅ፣ ሳቅስ መች ለምጄ?
በጭጋግ ታፍኜ፣
በጉም ተጀቡኜ፣
በዶፍ ተወልጄ፡፡”
አትበል ወዳጄ፡፡
* * *
በጉም መሃል እንጅ - የወጣችው ፀሐይ
ነፍስን እያሳሳች - ሀሴት የምታሳይ
ብቻዋን ስትቆም - በጠራራው ሰማይ
ንዳድ ሀሳብ ዘርታ - ባሳር ምታጋይ፡፡
ብቻ ሲሆንማ - ሳቅም ጠራራ ነው፤
ጥርስን ያራቆተ - የከንፈርህ ግዳይ፡፡

ቅርብኝ
ኖኅን መሰኘት አምሮህ - ታንኳ ቢጤ ስትገነባ
አምላክ ያዘዘህ ቀርቶ - ወዳጅህ መርከብህ ከገባ
ዓለም የጨው ክምር ሆና - ፍጥረታቷ ሲረግፉ
ድንገት ታንኳህ ላይ ብገኝ - ነፍሴን አርዷት ዶፉ
ርግቧን መሆን አልሻም፤ ከጎንህ እንዳልገኝ
የትም እንደወጣሁ ልቅር፤ ላንተስ ቁራህን ያድርገኝ
(በቅርቡ በደሴ ከተመረቀው የገጣሚ አካል ንጉሴ “ፍላሎት (የነፍስ አሻራዎች)” 2006፤ የግጥም መድበል የተወሰዱ)


=========


ኢዮሀ!
ኢዮሀ!
አበባ ፈነዳ!
ፀሀይ ወጣ ጮራ፡፡
ዝናም
ዘንቦ
አባራ፡፡
ዛፍ
አብቦ
አፈራ፡፡
ክረምት መጣ ሄደ
ዘመን ተወለደ፡፡
ዓለም አዲስ ሆነ፡፡
ለሊት ሲነጋጋ
ጋራው ድንጋይ ከሰል
የተተረከከ ፍም እሳት ደመናው
ፀሐይ ያነደደው፡፡
ዓለም ሞቆ
ደምቆ፡፡
ብርሃን ሲያሸበርቅ
ጤዛው ሲያብረቀርቅ፤
ሕይወት ሲያንሰራራ
ፍጥረት ሲንጠራራ
ዘመን ተለወጠ መስከረም አበራ፡፡
“ኢዮሃ አበባዬ፡፡”
(ከገብረክርስቶስ ደስታ)

 

የኢትዮጵያ የጽንስና ማህጸን ሐኪሞች ማህበር..መሑሀ

አዲሱ አመት ..2007.. ዓ/ም ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የሰላም ፣የጤናና የብልጽግና እንዲሆን ይመኛል፡፡
የዘመን መለወጫን ምክንያት በማድረግ ከእለቱ ጋር የነበረ ገጠመኝ ልናስነብባችሁ ወደድን፡፡ በመሆኑም ተከታዩን እነሆ ለንባብ ፡፡
.....ነገሩ ያጋጠመኝ በ2006 ዓ/ም መግቢያ ጳጉሜ 4/2005 ነው፡፡ እኔ በእድሜዬ ገና ሰላሳው የገባሁ ስሆን እዩኝ እዩኝ የምል .....መሬቱን ሲረግጠው ድንጋዩ ይፈነቀላል የምባል እይነት ነኝ፡፡.. ታድያ ...አለባበሴን አሳምሬ በአዲስ ዘመን ዋዜማ ነበር ወደ ከተማው ብቅ ያልኩት፡፡ እኔ ወንደላጤ ነኝ፡፡ ቤተሰብ እንዳለው ሰው በግ ወይንም ዶሮ ከሚሸጥበት ሳይሆን ያመራሁት ወደ ልብስ ተራው ነበር፡፡ ብዙም ባይሆንም በመጠኑ ደመወዜ እንደልብ የሚያንቀሳቅሰኝ ነበር፡፡ ከአንድ ኃብታም ድርጅት ውስጥ በአስተዳደ ሩም ፣በእቃ ግዢነቱም ፣በጠቅላላ አገልግሎትነቱም ፣ባለጉዳይ በማነጋገሩም ፣ በመወ ሰኑም ፣በማስወሰኑም...ብቻ ሰውየው ሌላ ሰው መቅጠር ስለማይፈልጉ እኔን ብቻ ከላይ ከታች ስለሚያመላልሱ...እኔም ታድያ ደህና አድርጌ ነበር የተጠቀ ምኩበት፡፡ አሁን ግን አንድ ወር ሆኖኛል ስራዬን ከለወጥኩ.....
ወደ ዘመን መለወጫው ገጠመኝ ልመለስና የ2006/መግቢያ የልብስ ገበያ በዋጋው ብዙም የሚታማ አልነበረም፡፡ ታድያ እየዞርኩኝ ጫማ ስመለከት አንዲት ኮረዳ በድንገት ገጠመችኝ፡፡
... ያነሳሁትን ጫማ እጄ ላይ አይታ...እውይ ባባትህ ...ያምራል ...ብትለካውስ? አለችኝ፡፡
...እኔም ቀና ብዬ ስመለከታት የሆነች ቆንጆ ልጅ ናት፡፡ መለስ አድርጌም...ምን ያረጋል ቢያምር... የወደድሽው አንቺ እንጂ ...ስላት...ታድያ እኔ ከወደድኩልህ መች አነሰህ? አንተ ደግሞ ጉረኛ ነህ መሰለኝ...ብላ ከት ብላ ሳቀች፡፡ አ.አ.ይ እኔ እንኩዋን ጉረኛ አይደለሁም፡፡ ግን እውነ..ን ነውኮ ...ሌሎች አያምርም ቢሉኝስ...ዋጋው ደግሞ ውድ ነው አልኩዋት፡፡
...እንገግዲህ...አለችኝና ትታኝ ወጣች፡፡ እኔ ግን አብሮአት ልቤ ሸፈተ፡፡ ጫማውን መግዛቱን ትቼ እሱዋን ተከተልኩዋት፡፡
..እኔ የምልሽ...
- ምንድነው የምትለኝ...
..የአዲስ አበባ ልጅ ነሽ?...
ከት ብላ ሳቀች፡፡ ምነው? አልኩዋት
- እንጃ...ጥያቄህ አስቆኝ ነዋ...መልሱዋ ነበር፡፡
..ምን ያስቃል...ሁኔታሽ...ንግግርሽ...ሁሉ ደስ ብሎኝ ነውኮ...
- ከአዲስ አበባ ውጭ ያለ ሰው እንደእኔ አይናገርም? አለችኝና ወዲያው
በማስከተል ...ዋናው ነገር... ጫማውን ገዛኸው? አለችኝ፡፡
..አንቺ ትተሸኝ ስትሄጂ ተውኩት...
- ለምን?
..እንዳታመልጪኝ... ልከተልሽ ...ብዬ ነዋ...
- በል ...ና እንሂድና መጀመሪያ ጫማውን ግዛና ከዚያ በሁዋላ እናወራለን...አለችኝ፡፡
በዚህ መልክ ነበር የእኔና የሜላት ግንኙነት የተጀመረው፡፡ ከዚያም ለአንድ ሶስት ወር ገደማ ሻይ ቡና እየተባባልን ቆየን፡፡ ሜላት በጣም ጨዋ ልጅ ነች፡፡ የሰው ገንዘብ በፍጹም አትፈልግም፡፡ አንድ ነገር ላድርግልሽ ስላት ፍጹም ፍቃደኛ አይደለችም፡፡ ለምንበላው ምግብ እንኩዋን ቢያንስ ሻይ ቡናውን ካልቻለች አይመቻትም፡፡ በቃ ...ለትዳር ጉዋደኛ የምትሆነኝ ልጅ አገኘሁ...የእንቁጣጣሽ ስጦታዬ ነች ብዬ አሰብኩ፡፡ ለእናት እና አባ.. ሁኔታውን አጫወትኩዋ ቸው፡፡ ቤተሰቤ በሙሉ ተደሰተ፡፡ መቼ ነው ታድያ ሽማግሌ የምንልከው የሚለው ጭቅጭቅ ከቤተሰቤ እያየለ ሲመጣ እስቲ ቆይ... ከእርሱዋ ጋር እኮ ገና አላወራነውም...እኔ የእራሴን ፍላጎትና ግምት ነው የነገርኩዋችሁ...አልኩዋቸው፡፡
...አንድ እሁድ እኔና ሜላት ለምሳ ቀጠሮ ያዝን፡፡ አብረን እየተመገብን እያለን...ላጎርሳት ስሞክር ...አአይ...አለችና ፊቷ ቅጭም አለ፡፡
..ምነው?...የእኔ ጥያቄ ነበር...
- አአይ...እኔ ጉርሻ አልወድም...
..ለምን?
- አባ..ን ስለሚያስታውሰኝ...ሰው ሲያጎርሰኝ አልወድም...
ለካንስ አባትዋ ሞተዋል፡፡ አዘንኩኝ፡፡ እንደገና ሀሳቤን ሰብሰብ አደረግሁና...
..አኔ የምልሽ...
- እህ...
..ለምን... እ.....ስላት... ገና ሀሳቤን ሳልቋጭ...
-ገብቶኛል ልትለው የፈለግኸው ነገር ገ ብ ቶ ኛ ል... አለችኝ፡፡
.. ታድያ ...ምን ችግር አለው?
-ምንም ችግር የለውም፡፡ ነገር ግን እኔ እነግርሀለሁ፡፡ አለችኝ፡፡
የዚያን እለት በዚሁ ተለያየን፡፡ ከዚያ በሁዋላ ስልክ ብደውል ...ቀድሞ ሳገኛት የነበረበት ካፊ..ሪያ እና ምግብ ቤት ብሔድ...ማንም...ምንም መረጃ ሊሰጠኝ አልቻለም፡፡ አጣሁዋት፡፡ግራ ተጋባሁ፡፡ በጣም ፈለግሁ ዋት...አላገኘሁዋትም፡፡ ጉዋደኛዋን ቤተሰብዋን...ማንንም አላውቅም፡፡ ታመምኩ ፡፡ አድራሻ አልሰጠችኝም፡፡ የት ነው የምትሰሪው ስላት በግልዋ እየተዟዟረች እንደም ትሰራ ነው የነገረችኝ፡፡ እንዲሁ ...ስጨነቅ... ስጨነቅ... ግንቦት 15/2006 /አንድ መልእክት ደረሰኝ፡፡ እንዲህ ይላል...
.....በድንገት ገበያ ላይ የገኘሁህ ወድ ጉዋደኛዬ...እንደምን ሰነበትክ፡፡ ድንገት ስለጠፋሁብህ በመጠኑም ቢሆን እንደጎዳሁህ ይሰማኛል፡፡ ስሜትህን እንዳልጎዳ ብዬ እንጂ እኔ ሚስት ለመሆን ቀርቶ ከወንድ ጋር እንኩዋን ለመገናኘት ገና በሕክምና የማስተካክለው የጤና ጉዳይ ስለነበረኝ አልደፍርም ነበር፡፡ በቤተሰብ አባል ተደፍሬ ...በድብቅ ...በህገ ወጥ መንገድ ጽንስ በማቋረጥ ምክንያት ማህጸኔ ተጎድቶ ስለነበር ለሕክምና ወደ ሆስፒታል መግባት ነበረብኝ፡፡ የመጨ ረሻ ምሳ የበላን ማግስት ነበር ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የገ ባሁት፡፡ ያንን የምሳ ቀጠሮ ብመለስም ባልመለስም ብዬ ሆን ብዬ ነበር ያመቻቸሁት፡፡ አሁን ሕክምናዬን ጨርሼ እቤ.. ገብቻለሁ፡፡ ከፈለግህ ጠይቀኝ፡፡ ላለፈው ይቅርታ አድር ግልኝ፡፡ አሁን እግዚአብሔር ይመስገን ጤነኛ ነኝ፡፡..... ይላል ...በመልእክተኛ የመጣው ደብዳቤ፡፡
እጅግ በጣም ነበር ያዘንኩትም ...የተደሰትኩትም፡፡ ታማ ሆስፒታል በነበረችበት ወቅት ከጎኗ ብሁን ኖሮ እወድ ነበር፡፡ ነገር ግን ያንን እድል አልሰጠችኝምና አዘንኩ፡፡ በሌላ በኩል... ከሕመሙዋ ድና በመውጣቷ ደግሞ በጣም ተደሰትኩ፡፡ ለማንኛውም ሁኔታዋን ለማየት በሰ ጠችኝ አድራሻ ከቤትዋ ሄጄ አገኘሁዋት፡፡ ተቃቅፈን ተላቀስን፡፡ ለካንስ እርሱዋም ወድዳኝ ነበር፡፡ ጭራሽ ፍቅሬ በረታ፡፡ በእቅፍዋ ስር እንድሆን...በእቅፌ ስር እንድትሆን ሁለታችንም ወደድን፡፡
እነሆ...በተገናኘን በአንድ አመታችን...ዛሬ መስከረም 3/2007 ዓ/ም ሰርጋችን ነው፡፡
.....ደስ ብሎናል ...ደስ ይበላችሁ....
ይስሐቅ ብርሐኔ/ከአዲስ አበባ/መሳለሚያ

Saturday, 13 September 2014 13:42

አገኘሁ አዳነ - ጣምራ ጠቢብ

         ተወልዶ ያደገው ጎንደር ነው፡፡ በአባቱ የሥራ ጸባይ ምክንት በልጅነቱ አሥመራን፣ አቆርዳትን፣ ተሰኔን ጨምሮ ወደተለያዩ አካባቢዎች ተጉዟል፡፡ እናቱ በልጅ አስተዳደግ በጣም ጥብቅ በመሆናቸው ከቤት እንዲወጣ የሚፈቀድለት ወይ ወደ ትምህርት ቤት፣ ወይ ወደ ቤተክርስቲያን ብቻ ነበር፡፡ ያንን ዘመን ሲያስታውስ በኪነ ቅብ ሥራዎች ያሸበረቀችውን ሎዛ ማርያም ቤተክርስቲያንን ያነሳል፡፡ ዓይኑም ልቡም፣ ቀልቡም በሥዕል ሕብረ ቀለም የተወጋው ያኔ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ከዚያ ሕፃናት አምባ ገባ፡፡ አምባ የፈለግከውን ለመሆን ነገሮች የተመቻቹበት፣ ነፃነት ያለበት አካባቢ እንደነበር ይናገራል፡፡ አጥር ተበጅቶለት ላደገው አገኘሁ ሕፃናት አምባ የተመቸ ሥፍራ ሆነለት፡፡ አንድ ቦታ ላይ በትኩረት መቆየትን፣ ማንበብን፣ ማስተዋልን ቀድሞ ስለሚያውቃቸው በመጣበት መንገድ ቀጠለ፡፡ ለዛሬ ማንነቱ ያ ዘመን እርሾ እንደሆነውም አይጠራጠርም፡፡
ሠዓሊ አገኘሁ አዳነ ከመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት አንስቶ ሥዕልን ይሞክር ነበር፡፡ ዕድለኛም ስለነበር ከልጅነቱ ምርጥ ምርጥ የሚባሉ መምህራን ገጥመውታል፡፡
አገኘሁ ከልጅነቱ ጀምሮ ጠያቂ ባህሪይ እንደነበረው ያስታውሳል፡፡ አራተኛ ክፍል እያለ የሥዕል መምህሩ በውሃ ቀለም ይሥላል፡፡ ከደቂቃዎች በኋላ አገኘሁ ያየውን ማመን አልቻለም፡፡ እጅጉን ተደነቀ፡፡
“የሚገርም ዓይነት፣ ዓይኑ እሳት የሚተፉ ጥቁር ሰውዬ ሳለ፡፡ ‘እንዴት ውሃ ሰው ይሆናል?’ ‘እንዴት ከሰው ዓይን እንደዚህ ዓይነት ኃይል የበዛበት ብርሃን ይረጫል?’ ስል በመደነቅ የጠየኩትን መቼም አልረሳውም፡፡”
የአገኘሁ ውስጣዊ ፍላጎት፣ ተሰጥዖውና ችሎታው እንዳለ ሆኖ ህፃናት አምባ ያንን የሚያለመልም ውሃ፣ አፈር እና ብርሃን እንደሆነው ይጠቅሳል፡፡ አገኘሁ ራሱን ወደ መንፈሳዊ ሰው አስጠግቶ ያስባል፡፡ ከአራት ማዕዘን ግድግዳ ውጪ ያለን ነገር የሚናፍቅ፣ በገሃድ የሚታይ፣ የሚጨበጠው የሚሰለቸው ዓይነት ሰውም ይመስላል፡፡
ሠዓሊነቱን ሳይቀር ወደዚ ቢወስደው ይወዳል፡፡ “ከሚዳሰስ እውነት ነገረ-ተረትን፤ ከዕለት ዜና ተረትን ልወድ እችላለሁ፡፡ ያለቀና የሚያልቅ ነገር ይሰለቸኛል፡፡ አገኘሁ ሠዓሊ ብቻ አይደለም፡፡ ገጣሚም ነው፡፡ “ጨለማን ሰበራ” እና “ለምን?” የተሰኙ ሁለት መድበሎች አሳትሟል፡፡ በባህርይው ማዳመጥ ደስ እንደሚለው የሚናገረው አገኘሁ አለማዊ ሰው ባይሆንም ይመስላል፡፡
“ሰውን ብደግፍ፤ ክርስቶሳዊ ስብዕና ቢሮረኝ እወዳለሁ፡፡ ማለም፣ ከሃሳብ ጋር መጫወት ደስ ይለኛል፡፡” ሠዓሊ አገኘሁ አዳነ ስፔይንን፣ ሆላንድን፣ ፈረንሳይን፣ ጀርመንን ፖርቹጋልን እና ቤልጂየምን ገብኝቷል፡፡ በነበረው ቆይታም ብዙ ነገሮችን ስለመማሩ ይናገራል፡፡
“በራሴ ፍጹምነት ታስሬ እንደነበር ተገንዝቤአለሁ፡፡ ለምለሚቷ ሀገሬ የሚለውን ሳይቀር ቀንሼአለሁ፡፡ ምክንያቱም በሌላው ሀገር ሃሪፍ ነገር ስላለ፡፡” ሠዓሊ አገኘሁ ባለትዳር እና የሦስት ልጆች አባት ነው፡፡ ቤተሰቦቹ ለሁለመናው ብርታቱ እንደሆኑም ይጠቅሳል፡፡
አገኘሁ ከልጅነቱ መምህርነትን ይመኝ ነበር፡፡ እንደፈለገው ግን ፈጥኖ አላገኘውም፡፡ በተለያዩ መሥሪያ ቤቶች ሲሰራ ቆይቶ ቢዘገይም ከመምህርነት ጋር ተገናኝቷል፡፡ ዛሬ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ ፈለገ ሰላም የሥነ-ጥበብ እና ዲዛይን ት/ቤት መምህር ነው፡፡ ሠዓሊ አገኘሁ አዳነ ወደፊት ወደ መፈውሰ ጥበብ ወይም ‘Art Therapy’፣ ‘Physical Therapy’፣ ‘Spritual Therapy’ ቢገባ ደስ እንደሚለው፣ ሥዕሉንም ቢሆን ከሰው ልጅ ጋር በቀጥታ እንዲገናኝ ማድረግ ቢችል ደስ ይለዋል፡፡
ምንጭ፡- ነቢይ ግርማ፣ “ጋለሪያ ቶሞካ አገኘሁ አዳነን ያቀርባል” (2007 ዓ.ም) በሚለው መጽሄት ላይ ያሰፈረው፡፡

Saturday, 13 September 2014 13:20

የዛሬ 40 ዓመት፡፡

(መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም)
… መስከረም ሁለትን ሳስብ ብዙ ነገር ወደ አዕምሮዬ ይመጣል፡፡ ደርግ ከንጉሰ ላይ ሥልጣን ከተረከበ በኋላ በየዓመቱ መስከረም ሁለት ትልቅ ክብረበአል ነበር፡፡ ወጣቱ አብዮት የሚባለውን ሲያይ መጀመሪያ አካባቢ ጉጉና ደስተኛ ነበር፡፡ በአሉም በሠራዊቱ የተለያዩ ትርኢቶች ታጅቦ፣ በየአመቱ በአብዮት አደባባይ (መስቀል አደባባይ) በከፍተኛ ድምቀት ይከበር ነበር፡፡ ወታደሩ ከ4-5 ሰአት የሚዘልቅ ትርኢቶችን ያቀርባል፡፡ በታላቁ ቤተ-መንግስትና በብሔራዊ ቤተመንግስትም በእለቱ ጓድ መንግሥቱ ኃለማርያም እና ባለቤታቸው ወ/ሮ ውብአንቺ ቢሻው በተገኙበት ለሁሉም የቤተመንግስቱ ጠባቂዎች ታላቅ ግብዣ ይደረግ ነበር፡፡
መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም ደግሞ ሲታወስ ደርግ አዋጁን ከተናገረ በኋላ፣ ህዝቡ የእርስ በእርስ ግጭት ጠብቆ ነበር፡፡ ከፍተኛ እልቂት ይመጣል ተብሎ ተሠግቶ ነበር፡፡ ታንኮችና መትረየስ የጫኑ ተሽከርካሪዎች ይርመሰመሱ ነበር፡፡ ሰው መተያየት ፈርቷል፣ መኪናዎቹንና ታንኮቹን ቀና ብሎ ማየት ፈርቷል፡፡ ሰው በአጠቃላይ እርስ በእርስ ተፈራርቷል፡፡ ምናልባት ሌሊት አሜሪካን በአውሮፕላን ወረራ ፈጽማ ወይም እስራኤል መጥታ ንጉሱን ይወስዳሉ የሚሉ ሃሳቦች በፍራቻ መሃል ይንሸራሸሩ ነበር፡፡
ክቡር ዘበኛ እና ወታደሩ ሊጋጭ ይችላል የሚል ስጋትም ነበር፡፡ ነገር ግን ክቡር ዘበኛ ምንም የወሰደው እርምጃ የለም፡፡ የመሣሪያ ድምጽ እንኳ በእለቱ ኮሽ አላለም፡፡ መውረዳቸውን አምኖ ተቀብሏል፡፡ ይህ ባይሆን እንኳ መፈንቅለ መንግስት አድራጊው ወገን፣ ክቡር ዘበኛ ካንገራገረ ማጥቃት የሚችል ሠራዊት በቤተ-መንግስቱ በድብቅ ተዘጋጅቶ ነበር፡፡
ንጉሡ ከቤተ-መንግስታቸው በደርጉ ሃይሎች ተከበው፣ በተዘጋጀችለቸው ቮልስዋገን መኪና ውስጥ ገብተው ወደ 4ኛ ክ/ጦር ሲወሰዱ፣ ብዙ ህዝብ በመንገድ ላይ ወጥቶ ይመለከት ነበር፡፡ በእድሜ ጠና ባሉት ሰዎች ላይ የማዘን ስሜት ይስተዋል ነበር፡፡ ወጣቱ ደግሞ “ሌባው! ሌባው! ሌባው!” የሚል ስድብ በፉጨትና በጩኸት እያጀበ ይሰነዝራል፡፡ ወጣቱ በጣም ይሳደብ ነበር፡፡ በተለይ ቮልስዋገኗ መስቀል አደባባይ አካባቢ ስትደርስ የነበረው ፉጨትና ጭብጨባ ልዩ ነበር፡፡
ደርጉ ዋና ዋና የሚባሉትን የመንግስት ስልጣኖች በሚገባ በቁጥጥሩ ስር ከዋለ በኋላ ስለነበር እሣቸውን ከስልጣን ያወረደው መንገዱ ሁሉ የቀና ሆኖለታል፡፡ ጃንሆይም ይህን ስለሚያውቁ በአጋዦቻቸው አማካይነት ሌላ እርምጃ ለመውሰድ አላንገራገሩም፡፡ ዝም ነው ያሉት፡፡ ወደ ቮልስዋገኗ እንዲገቡ ሲጠየቁ አላንገራገሩም፡፡ ለምን በቮልስዋገን ተወሰዱ? ተብሎ ሲታሰብ ደርግ እሣቸው መሆናቸው ሳይታወቅ እንዲሄዱ የተጠቀመበት ቴክኒክ ነበር፡፡ ተራ ሰው እንዲመስሉና ግርግር እንዳይፈጠር ነው፡፡ ነገር ግን ሰው አውቆታል፡፡ በኋላ ዳርና ዳር መትረየስ የጫኑ ጂፖች አጅበዋቸው ሲሄዱ ሰው ከፉጨትና ጭብጨባ፣ ስድብ በቀር አንዲት ጠጠር እንኳ አንስቶ አልወረወረም፡፡ በዚያ ላይ ደህንነቱ በሰው መሃል ተሰግስጓል፡፡ ወታደሩም አንዳንዱ ሲቪል ለብሷል፡፡ ጃንሆይ ከስልጣን ከወረዱ በኋላ በእውነቱ ምስኪናዊ ህይወት ነው ያሳለፉት፡፡ ማንም ጠያቂ የላቸውም ነበር፡፡ የሚቀርባቸውም ሰው አልነበረም፡፡ ብቻቸውን አንድ ቤት ውስጥ ነበር የሚኖሩት፡፡ ንጉሱ ዘወትር ፊታቸውን ወደ ቤተክርስቲያኑ አዙረው ፀሎት ሲፀልዩ ስታይ በጣም ያሳዝኑ ነበር፡፡ ማንም አያናግራቸውም፤ አይጠጋቸውም ነበር፡፡ አንዲት ምግብ የምታበስል ልጅ አለች፤ እሷም ብትሆን በተወሰነ ሰዓት መጥታ ስራዋን ሰርታ ነው የምትሄደው፡፡ አርብ እና አሮብን ጠንቅቀው ይፆሙ ነበር፡፡ ልጅቱም ዘግይታ ነው ምግብ የምትሰራላቸው፡፡ ልጅቱ ልብሱን አዘጋጅታላቸው ትሄዳለች፡፡ ራሳቸው ይለብሳሉ፡፡ በዚህ መልኩ በዚያው በቤተ መንግስቱ በቀን እስረኝነት ከሰው ተገልለው ሲኖሩ ከቆዩ በኋላ ህይወታቸው ማለፉ ተነገረ…
(“ህይወት በመንግስቱ ቤተ-መንግስት” የተሰኙ ተከታታይ መፅሃፎች ደራሲና የቀድሞ ልዩ ሃይል አባል ወ/ር እሸቱ ወንድሙ ለአዲስ አድማስ ከፍተኛ ሪፖርተር አለማየሁ አንበሴ መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም አስመልክቶ ከሰጡት ቃለ ምልልስ የተወሰደ፡፡)

Saturday, 13 September 2014 13:20

የዛሬ 40 ዓመት፡፡

(መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም)
… መስከረም ሁለትን ሳስብ ብዙ ነገር ወደ አዕምሮዬ ይመጣል፡፡ ደርግ ከንጉሰ ላይ ሥልጣን ከተረከበ በኋላ በየዓመቱ መስከረም ሁለት ትልቅ ክብረበአል ነበር፡፡ ወጣቱ አብዮት የሚባለውን ሲያይ መጀመሪያ አካባቢ ጉጉና ደስተኛ ነበር፡፡ በአሉም በሠራዊቱ የተለያዩ ትርኢቶች ታጅቦ፣ በየአመቱ በአብዮት አደባባይ (መስቀል አደባባይ) በከፍተኛ ድምቀት ይከበር ነበር፡፡ ወታደሩ ከ4-5 ሰአት የሚዘልቅ ትርኢቶችን ያቀርባል፡፡ በታላቁ ቤተ-መንግስትና በብሔራዊ ቤተመንግስትም በእለቱ ጓድ መንግሥቱ ኃለማርያም እና ባለቤታቸው ወ/ሮ ውብአንቺ ቢሻው በተገኙበት ለሁሉም የቤተመንግስቱ ጠባቂዎች ታላቅ ግብዣ ይደረግ ነበር፡፡
መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም ደግሞ ሲታወስ ደርግ አዋጁን ከተናገረ በኋላ፣ ህዝቡ የእርስ በእርስ ግጭት ጠብቆ ነበር፡፡ ከፍተኛ እልቂት ይመጣል ተብሎ ተሠግቶ ነበር፡፡ ታንኮችና መትረየስ የጫኑ ተሽከርካሪዎች ይርመሰመሱ ነበር፡፡ ሰው መተያየት ፈርቷል፣ መኪናዎቹንና ታንኮቹን ቀና ብሎ ማየት ፈርቷል፡፡ ሰው በአጠቃላይ እርስ በእርስ ተፈራርቷል፡፡ ምናልባት ሌሊት አሜሪካን በአውሮፕላን ወረራ ፈጽማ ወይም እስራኤል መጥታ ንጉሱን ይወስዳሉ የሚሉ ሃሳቦች በፍራቻ መሃል ይንሸራሸሩ ነበር፡፡
ክቡር ዘበኛ እና ወታደሩ ሊጋጭ ይችላል የሚል ስጋትም ነበር፡፡ ነገር ግን ክቡር ዘበኛ ምንም የወሰደው እርምጃ የለም፡፡ የመሣሪያ ድምጽ እንኳ በእለቱ ኮሽ አላለም፡፡ መውረዳቸውን አምኖ ተቀብሏል፡፡ ይህ ባይሆን እንኳ መፈንቅለ መንግስት አድራጊው ወገን፣ ክቡር ዘበኛ ካንገራገረ ማጥቃት የሚችል ሠራዊት በቤተ-መንግስቱ በድብቅ ተዘጋጅቶ ነበር፡፡
ንጉሡ ከቤተ-መንግስታቸው በደርጉ ሃይሎች ተከበው፣ በተዘጋጀችለቸው ቮልስዋገን መኪና ውስጥ ገብተው ወደ 4ኛ ክ/ጦር ሲወሰዱ፣ ብዙ ህዝብ በመንገድ ላይ ወጥቶ ይመለከት ነበር፡፡ በእድሜ ጠና ባሉት ሰዎች ላይ የማዘን ስሜት ይስተዋል ነበር፡፡ ወጣቱ ደግሞ “ሌባው! ሌባው! ሌባው!” የሚል ስድብ በፉጨትና በጩኸት እያጀበ ይሰነዝራል፡፡ ወጣቱ በጣም ይሳደብ ነበር፡፡ በተለይ ቮልስዋገኗ መስቀል አደባባይ አካባቢ ስትደርስ የነበረው ፉጨትና ጭብጨባ ልዩ ነበር፡፡
ደርጉ ዋና ዋና የሚባሉትን የመንግስት ስልጣኖች በሚገባ በቁጥጥሩ ስር ከዋለ በኋላ ስለነበር እሣቸውን ከስልጣን ያወረደው መንገዱ ሁሉ የቀና ሆኖለታል፡፡ ጃንሆይም ይህን ስለሚያውቁ በአጋዦቻቸው አማካይነት ሌላ እርምጃ ለመውሰድ አላንገራገሩም፡፡ ዝም ነው ያሉት፡፡ ወደ ቮልስዋገኗ እንዲገቡ ሲጠየቁ አላንገራገሩም፡፡ ለምን በቮልስዋገን ተወሰዱ? ተብሎ ሲታሰብ ደርግ እሣቸው መሆናቸው ሳይታወቅ እንዲሄዱ የተጠቀመበት ቴክኒክ ነበር፡፡ ተራ ሰው እንዲመስሉና ግርግር እንዳይፈጠር ነው፡፡ ነገር ግን ሰው አውቆታል፡፡ በኋላ ዳርና ዳር መትረየስ የጫኑ ጂፖች አጅበዋቸው ሲሄዱ ሰው ከፉጨትና ጭብጨባ፣ ስድብ በቀር አንዲት ጠጠር እንኳ አንስቶ አልወረወረም፡፡ በዚያ ላይ ደህንነቱ በሰው መሃል ተሰግስጓል፡፡ ወታደሩም አንዳንዱ ሲቪል ለብሷል፡፡ ጃንሆይ ከስልጣን ከወረዱ በኋላ በእውነቱ ምስኪናዊ ህይወት ነው ያሳለፉት፡፡ ማንም ጠያቂ የላቸውም ነበር፡፡ የሚቀርባቸውም ሰው አልነበረም፡፡ ብቻቸውን አንድ ቤት ውስጥ ነበር የሚኖሩት፡፡ ንጉሱ ዘወትር ፊታቸውን ወደ ቤተክርስቲያኑ አዙረው ፀሎት ሲፀልዩ ስታይ በጣም ያሳዝኑ ነበር፡፡ ማንም አያናግራቸውም፤ አይጠጋቸውም ነበር፡፡ አንዲት ምግብ የምታበስል ልጅ አለች፤ እሷም ብትሆን በተወሰነ ሰዓት መጥታ ስራዋን ሰርታ ነው የምትሄደው፡፡ አርብ እና አሮብን ጠንቅቀው ይፆሙ ነበር፡፡ ልጅቱም ዘግይታ ነው ምግብ የምትሰራላቸው፡፡ ልጅቱ ልብሱን አዘጋጅታላቸው ትሄዳለች፡፡ ራሳቸው ይለብሳሉ፡፡ በዚህ መልኩ በዚያው በቤተ መንግስቱ በቀን እስረኝነት ከሰው ተገልለው ሲኖሩ ከቆዩ በኋላ ህይወታቸው ማለፉ ተነገረ…
(“ህይወት በመንግስቱ ቤተ-መንግስት” የተሰኙ ተከታታይ መፅሃፎች ደራሲና የቀድሞ ልዩ ሃይል አባል ወ/ር እሸቱ ወንድሙ ለአዲስ አድማስ ከፍተኛ ሪፖርተር አለማየሁ አንበሴ መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም አስመልክቶ ከሰጡት ቃለ ምልልስ የተወሰደ፡፡)

የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የግል አሽከርና አልባሽ ስዩም ጣሰው በ14 ዓመት የቤተመንግስት አገልግሎታቸው፣ በዕለት ማስታወሻቸው ላይ ሲያሰፍሩ የቆዩትን መረጃ ጋዜጠኛ ግርማ ለማ አስተካክሎ በ2006 ዓ.ም “የንጉሡ ገመና” በሚል ለንባብ አብቅቶታል፡፡ የጃንሆይ የመጨረሻ ሰዓት ምን እንደሚመስል ለማስታወስ ከዚሁ መጽሐፍ ላይ ተከታዩን ቀንጭበን አቅርበናል፡፡ ጃንሆይ ከስልጣን የወረዱት መስከረም 2 ቀን 1967 ዓ.ም ነው - የዛሬ
40 ዓመት፡፡

…እርሳቸውም የተቀበሉት ከልብ ነው፡፡ ማታ የሻምበል ደምሴ የክብር ዘበኛ ንዑስ ኮሚቴ ሊቀመንበር ከጀ/ፍሬሰንበት ቢሮ ድረስ መጥቶ አቶ ክበበው ኃይሌንና አቶ ወንደሰን አንዳርጌን አነጋግሮአል፡፡ ይኸውም ግርማዊነታቸው ምናልባት ሕይወታቸውን በገዛ እጃቸው እንዳያጠፉ በአጠገባቸው የሚገኘውን መሣሪያና መድኃኒቶች በሙሉ እንዲያሸሹ ነግሮአቸው ሄደ፡፡ እነርሱም መድኃኒት ይኑር አይኑር ስለማያውቁ፣ መሳሪያው ብቻ ከአጠገባቸው ወደሌላ ኰሜዲኖ ውስጥ ተዛውሮ እንዲቀመጥ አደረጉ፡፡ እኔም ወደ ቤቴ ሄድኩ፡፡
በ2/1/67 ዓ.ም ጠዋት አድሚራል እስክንድር መጥተው፤ “አዋጅ ስለአለ ሬዲዮ ይከፈትላቸው” ስላሉ ገብተው፣ ሬዲዮ በ1፡30 ሰዓት ሲከፈት ሳይሠራ ትንሽ ቆየት ብሎ ግርማዊነታቸው ከሥልጣን መውረዳቸውን ሲያውጅ፣ ጃንሆይም “ወይ አንተ እግዚአብሔር” ብለው በጥሞና እስከመጨረሻው ድረስ አደመጡ፡፡ ከዚያም ትንሽ ቆይተን ከመኝታ ቤት ወደ ውጭ ወጣን፡፡
ከትንሽ ደቂቃዎች በኋላ አድሚራል እስክንድር መጥተው ጠሩንና ገባን፡፡ ከዚያም ልብስ መልበስ ጀመሩ፡፡ በሚለብሱበት ጊዜ ከመጥቆራቸው በስተቀር ከሰሞኑ ምንም ለውጥ አላሳዩም፡፡ ለብሰው ከጨረሱ በኋላ ፀሎት ለማድረስ ስለቆሙ ትተናቸው ወጣን፡፡ ፀሎት እንደጨረሱ 2፡10 ሰዓት ሲሆን በረንዳ ወጥተው ከተንሸራሸሩ በኋላ፣ ወደ ውስጥ ተመልሰው ከአሽከሮች መኝታ ቤት ሲደርሱ ልዕልት ሰብለ ደስታና ወ/ሮ ሜሪ አበበ ከአድሚራል እስክንድር ጋር ሲመጡ አገኙዋቸው፡፡ እጅ ነስተው ሳሙዋቸው፡፡ ከዚያም ተያይዘው ወደ መኝታ ቤት ገቡ፡፡ ከዚያም አድሚራል መጡና “ቁርስ ገበታ ቤት ከሚሆን መኝታ ቤት ቢሆን ይሻላል” ስላሉ ለቦዮቹ ነገርንና ወደዚያው ተዘጋጅቶ፣ ቁርስ በተለመደው ሰዓት 2፡20 ሰዓት ቀረበ፡፡
እርሳቸውም ከተዘጋጀላቸው ከመልበሻ ቤት ገቡና ተቀመጡ፡፡ ሲያዩዋቸው ታዲያ የመዝናናት መልክ ነበራቸው፡፡ ቁርሳቸውንም ከወትሮው ባልተለየ ሁኔታ በሉ፡፡ እንደውም ከውሻቸው ጋር እየቀለዱ ሥጋ ሲያጐርሱ፣ ሲስቁ በጣም ገረመኝ፡፡ እንኳን ከሥልጣን የወረዱ ምንም የሆኑ አልመሰላቸውም ነበረ፡፡ ቁርስ በልተው እንደጨረሱ ፀሎት አደረሱና በ 2፡38 ወደ ሳሎን ወጡ፡፡
በ2፡43 ሰዓት ደግሞ ከመኝታ ቤት ተመለሱና እቢሮአቸው ቁጭ ብለው “ቦርሳዬን አምጣልኝ” አሉኝና ወስጄ ሰጥቼ ሲከፍቱት ወጣሁ፡፡ ትንሽ እንደቆየሁ አንድ ነገር ተሰማኝ፡፡ ይኸውም ምናልባት መድኃኒት ከቦርሳቸው ውስጥ አስቀምጠው እንደሆነ አውጥተው የጠጡ እንደሆነ ብዬ ስለተጠራጠርኩ፣ አድሚራልን ጠርቼ ገብተው ከእርሳቸው ጋር እንዲቆዩ ስለነገርኳቸው፣ ከእህቶቻቸው ጋር ተያይዘው ገቡ፡፡
እነርሱም ሲገቡ ቦርሳቸውን ከፍተው ከውስጡ ዕቃ ይፈልጉ ነበር፡፡ መሳሪያቸውን ግን ማታ ካደረበት ቦታ አንስተው ከዱሮው ቦታ አሽከሮቹ መልሰው አስቀምጠውት ስለነበር፣ ለፀሎት እንደቆሙ ተመካክረን፣ እኔ ሁለት ሽጉጥና አንድ በቦርሳ ውስጥ ያለ አውቶማቲክ ሽጉጥ (በጣም ትልቅ ነው) አወጣሁና፣ ከተረኛው አሽከር መኝታ ቤት ካለው የወረቀት መመርመሪያ ውስጥ አስቀመጥኩት፡፡ ስለዚህ ከመድኃኒት ሌላ መሳሪያ ስለሌለ የሰጋሁት መድኃኒት ይጠጣሉ ብዬ ነበር፡፡
ጃንሆይና ልዑል ራስ እምሩ ቢሮ ገብተው ትንሽ ቆይተው፣ በ4፡00 ሰዓት የደርጉ አባሎች በጀ/ኃይለጊዮርጊስ ተጠርተው ከቢሮ ገቡ፡፡ ወደዚያው ሠላምታ ሰጡና አንድ የፖሊስ ሠራዊት ባልደረባ ሻለቃ አዋጁን አነበበላቸው፡፡ ይኸው ሻለቃ በቀደም ስለውጭ አገር ገንዘብ መመለስ ጉዳይ ለመነጋገር የመጡት የደርጉ አባሎች መሪና ወረቀቱንም ያነበበው ደበላ ዲንሳ ነበር፡፡ አዋጁን ለማንበብና ጃንሆይን ይዘው ለመሄድ በገቡ ጊዜ፣ ከ8 ቀን በፊት የክብር ዘበኛ መረጃ ሠራተኞች በሻምበል ኃይሉ አዴሳ ኃላፊነት ለውስጥ ጥበቃ ተብሎ የገቡት፣ ከአሽከሮች መካከል እደርጐቹ ላይ አደጋ እንዳይጣል ቁጥጥራቸው ፍፁም ሌላ ነበር፡፡ ከውጭ ደግሞ ዙሪያውን ከፎቅ ሆኖ እንዳይተኮስባቸው መሳሪያዎቻቸውን ወደላይ አድርገው ይጠብቁ ነበር፡፡
ደርጐቹም ገብተው ጃንሆይን እስከተገናኙ ድረስ የነበራቸው መረበሽ ከባድ ነበር፡፡ ከቢሮ ተጠርተው ሲገቡ እያንዳንዳቸው ሙሉ ትጥቅ ነበራቸው፡፡ ፊልም አንሺዎች፣ ፎቶግራፍ አንሺዎች፣ የድምጽ መቅረጫ የያዙ ጋዜጠኞች፣ ሪፖርተሮችና የወታደር ጋዜጠኞች ጭምር አብረው ገብተዋል፡፡ ከጋዜጠኞች የማውቃቸው አቶ ማዕረጉ በዛብህ፣ አቶ ደበበ እሸቱ (የድምጽ መቅረጫ) የያዘ፣ አቶ ተፈሪ ብዙአየሁ (የቴሌቪዥን ፊልም አንሺ) መብራት የሚያበራውን ስሙን አላውቀውም እንጂ ለዚሁ ሥራ ብዙ ጊዜ ይመጣል፡፡ ሻለቃውም አዋጁን አነበበ፡፡ በሚያነብበት ጊዜ ኡዚውን ከደረቱ ላይ አንግቶ ነው፡፡
አዋጁ ሲነበብ ግርማዊነታቸው በጽሞና በደንብ ሁነው ያዳምጡ ነበረ፡፡ ከዘወትሩ አሁንም ምንም ለውጥ አላሳዩም ነበር፡፡
አዋጁን አንብቦ ሲጨርስ፣ ግርማዊነታቸው የተገለለ ቦታ እንደተዘጋጀላቸው ስለሆነ ከልዕልት ተናኘ ጋር እንዲቀመጡ ስለተወሰነ አብረዋቸው እንዲሄዱ ጠየቃቸው፡፡ እርሳቸውም ተዝናንተው ተቀመጡና “እኛ ለሀገራችን በጦርነትም ሆነ በሰላም ጊዜ ሠርተንላታል፡፡ እናንተም ይህን ጠንቅቃችሁ ታውቁታላችሁ” ብለው ንግግራቸውን ሳይጨርሱ፣ ወታደሮቹ አንድ ጊዜ ግር ግር አሉና ጋዜጠኞቹን በሙሉ አስወጡዋቸው፡፡ ጋዜጠኞቹ ከወጡ በኋላ ንግግራቸውን በእርጋታ በመጀመር፣ “መጀመሪያ የጦር ኃይላችንን በዘመናዊ መልክ ስናዘጋጅ፣ ይህ አሁን የደረሰው የመሳሰሉ ነገሮች እንደሚደርሱ አስቀድመን የተገነዘብነው ስለሆነ ለኛ አዲስ አይደለም፡፡ ነገር ግን የወታደር ተግባሩ ጠረፍን ከአጥቂ ጠላት መጠበቅ ሲሆን፤ አሁን እናንተ በከተማ ተቀምጣችሁ አላማችሁን በመርሳት የምታደርጉት ትክክል አይደለም፡፡
“ወታደር ለጠረፍ እንጂ መቼ ለከተማ” አሉዋቸውና አንዳንዶቹን እየጠሩ መጠየቅ ጀመሩ፡፡
አንዱን የአየር ኃይል ባልደረባ “ና” ብለው፤ “ዕድሜህ ስንት ነው? አገልግሎትህስ?” እያሉ ሲጠይቁ፣ እኛንም በዚያ አካባቢ የነበርነውን አባረሩን፡፡
ወደዚያው አድሚራል እስክንድር ከእህቶቻቸው ጋር ፎቅ ላይ ስለነበሩ አስጠሩኝና ወጣሁ፡፡ እርሳቸውም ጀ/ፍሬሰንበት ከአጠገባቸው በምንም ዓይነት እንዳይለይ ንገረው ብለውኝ እሺ አልኳቸውና ቆምኩ፡፡ ወደዚያው ወደ መኝታ ቤት ከወሰኔ ጋር ገብተን፣ በመስኮት ቁልቁል ስናይ አንዲት ቮልስዋገን መኪና ስትቀርብ አየንና ሊወስዱዋቸው ነው ብለን ሮጠን ስንወርድ፣ አድሚራል ተጠርተው ወርደው ጃንሆይም ሲወጡ ደረስን፡፡ ወደዚያው ጃንሆይ የሚረዳዎት አሽከር ስለሚያስፈልግ፣ እርስዎ ደስ የሚልዎትንና የሚረዳዎትን ይምረጡ ሲሉ፣ እርሳቸውም “ወሰኔ ይሁንልኝ” አሉና መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ ሲወጡም ዘወትር ለሽርሽር እንደሚወጡ ነበር፡፡
ወታደሮቹም ከግራና ቀኝ እንዲሁም ከኋላ አጅበዋቸው ነበር፡፡ ውጭ እንደወጡም የሹፌራቸው የጀ/ሉሉ ቮክስዋገን ቆማ ስለነበር፣ አጠገቧ ሲደርሱ ግራ ገባቸውና ቆሙ፡፡ ወደዚያው በሩ ሲከፈትላቸው ስለገባቸው ገቡ፡፡ በዚህ ጊዜ ውሾቻቸው አብረው ገቡ፡፡ ጐትተው አስወጡዋቸው፡፡ ከእሸቱ ጋር ጭቅጭቅ ተፈጠረ፡፡ በመጨረሻ ውሾቹን ታቅፎ ወደ ውስጥ አስገባቸው፡፡ በማግስቱ ዶክተር ግርማ መጥቶ ወሰዳቸው፡፡ በፊትም የሚያክማቸውና ሲያማቸውም እርሱ ቤት ነበር የሚሄዱት፡፡ እርሳቸው በቮክስዋገንዋ ሲሄዱ፣ አድሚራልን ደግሞ በትልቁዋ ኩምቢ ቮክስዋገን (የፖሊስ ናት) አስገብተው ወሰዱዋቸው፡፡ እኛም ተመልሰን እኔና ወሰኔ ዕቃ መክተት ጀመርን፡፡ ለኛ የመሰለን፣ የወሰዱዋቸው ግርማዊት ቪላ/የልዕልት ቤት/ ወይም ልዑል መኰንን ቤት እንጂ 4ኛ ክፍለ ጦር አልመሰለንም፡፡ ምክንያቱም የወጡት በ2ኛ በር ስለነበረ ነው፡፡ እኛም የሚያስፈልገውን ልብስ አዘጋጀን፡፡ ብዙውንም አውጥተን ከተትን፡፡ በዚህ ጊዜ የተቀሩት ቁጭ ብለው ይተክዙ ነበረ፡፡ አንዳንድ የሴት አሽከሮች ለዚያውም ድሆቹ ከሚያለቅሱ በስተቀር ከሌሎቹ አንድም የሚያለቅስ አልነበረም፡፡
በዚያ አካባቢም የተገኙት የበሉት ሳይሆኑ ድሆቹ ነበሩ፡፡ የበሉትማ ገና ዱሮ ወጥተው ዙሪያውን ያንዣብባሉ፡፡ በ5፡30 ሌሎች የደርግ አባሎች መጡና በጀ/ወርቁ የክብር ዘበኛ ተጠባባቂ አዛዥ አማካኝነት ከመኝታ ቤት ገቡ፡፡ ወደዚያው ቤቱንና ዕቃውን እየተመለከቱ፣ ግማሾቹ “መታሸግ አለበት” ሲሉ፣ ግማሾቹ ደግሞ የተለየ ሃሳብ ሲያቀርቡ፣ እኔና ወሰኔ ጀ/ወርቁን ዕቃ መክተት ያስፈልግ እንደሆነ ፈቃድ ጠየቅናቸው፡፡ እርሳቸውም “የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ ቶሎ ቶሎ አውጡ” ብለው ፈቀዱልንና ጨርሰን አወጣንና ከተትን፡፡ እነርሱም ቤቱ በመታሸጉ ተስማሙና ታሸገ፡፡ ለጃንሆይ የሚያስፈልግ ዕቃ ሲኖር ከእኛ ዘንድ ሁለት ወይም ሦስት ሰው እየመጣ፣ ከአሽከሮቹ ጋር ከፍተው ዕቃው ከወጣ በኋላ እንደገና ይታሸጋል ብለው ተስማሙና አሸጉት፡፡
ከመኝታ ቤት የደርጉ አባሎች በገቡ ጊዜ አብዛኛዎቹ የሐዘን ስሜት ነበራቸው፡፡ በተለይም አንድ የጦር ሠራዊት ባሻ እንባው መጥቶ ግጥም ሲልበት፣ እንዳይታይ ዞር ብሎ እንባውን ሲጠርግ አይቻለሁ፡፡ የዕቃውንም መመሰቃቀል አይተው፣ “ይኸ ሳይነካ እንዳለ መሆን አለበት” በማለት ምንም ሳይነኩ ወጡ፡፡ ከዚያም ወደ ሳሎንና ገበታ ቤት ሄደው ዕቃውን እያዩ ሲያሽጉ፣ በ6፡45 ሌሎች የደርጉ አባሎች አቶ መንበረ ወልደማርያምን ይዘው መጡ፡፡ ከዚያም በፊት መጥተው ያሽጉ የነበሩትን የደርጉ አባሎች ጠርተው እሽጉን አስከፍተው ከመኝታ ቤት ገቡ፡፡ ከዚያም ትልቁን የገንዘብ መያዣ ቦርሳ ከፍተው፣ ከውስጡ ያለውን ብርና ልዩ ልዩ ዶክሜንት ማየት ጀመሩ፡፡ ታዲያ የቦርሳው ቁልፍ ከጃንሆይ ቀለበት ሥር ነበርና ቀለበቱን አምጥተው ነው የከፈቱት፡፡ ከአንድ ፊት ያለው ግን በቁጥር የሚከፈት ስለሆነና ስለላላወቁት ግማሾቹ “ይቀደድ” ሲሉ፣ አንድ መኰንን ግን “ይህ መቀደድ አይገባውም፣ ለታሪክ መቀመጥ አለበት” ስላለ፣ በመፈልቀቅ በእጃቸው እየገቡ በጐን በኩል አወጡ፡፡ በ7፡10 ሰዓት ልብሱና ምግቡ ጃንሆይ ወደአሉበት ቦታ ሄደ፡፡ …ለዘመን መለወጫ በዓል የተዘጋጀው ግብር የቀረበው ለደርጉ አባሎች ነበር፡፡ በዚህ ጊዜ እነዚያ ሲያማቱና ለዚህ ውድቀት ያበቁዋቸው፣ ሲዘርፉ የነበሩት አንደኛቸውም አልነበሩ፡፡ እዚያ ተኩራምተው ሲያለቅሱና ሲያዝኑ የነበሩት ምንም ያልተደረገላቸው ድሆቹ ብቻ ነበሩ፡፡ የጦር ሠራዊት ባልደረባ፣ ወታደር፣ ሹፌር፣ መጡ፡፡ ከዚያም እኔ ዘንድ መጥተው ምንም የሄደ “ዕቃ ስለሌለ ልንወስድ ነው የመጣነው፡፡ በተለይም የሚያርፉበት አልጋ ስለሌለ ቶሎ ቢሰጠን” ብለው ጠየቁኝ፡፡ እኔም “አቶ ጥላሁን እኮ ገና ከሰዓት በፊት ሄዶአል” ብለውኛል፤ ምናልባት አላስገባ ብለዋቸው እንደሆነ ብላቸው “የለም ውሸት ነው!” አለኝ፡፡
በተለይም የ10 አለቃው በጣም በማዘን “እስከ አሁን እኮ ከአንዲት ትንሽ ወንበር ላይ ቁጭ ብለው ነው ያሉት፤ ምነው እንደው የሚያስብ ሰውም የለ እንዴ?” አለኝ፡፡ እኔም ወደዚያው ወደ ዕቃ ክፍሉ ያሉትንና የሚያሽጉትን የደርጉ አባሎች ሄጄ ባነጋግራቸው፤ “ለምን እስከአሁን አልሄደላቸውም?” ቢሉኝ ሰው ቸልተኛ ስለሆነ ከእናንተ ዘንድ የሚያስገድድ ይሰጠኝ፡፡ በተለይም የዚህን ሥራ/ፕሮሲጀር/ የሚያውቀው ሻለቃ ሳህሌ ስለሆነ ከአለበት ቦታ ተፈልጐ እንዲወሰድ ብዬ ለአንድ የክብር ዘበኛ ሻለቃ ስነግራቸው፣ እርሳቸውም አንድ መቶ አለቃ ከላይ ግቢ ወጥቶ ለወታደሩ ትዕዛዝ እንዲሰጥና ዕቃ የሚወስዱ ሰዎች እንዳይቸገሩና በተለይም የሚስቸግሩ ሰዎች እንዳሉ እንዲያስገድዱ ብለው ሰጡኝ፡፡
ግርማዊነታቸው 4ኛ ክፍለ ጦር እንደደረሱ ኪሳቸው ተፈትሾ ብዕር፣ ክራቫት፣ ብራስሌት፣ ቀበቶ… ቀለበታቸውን፣ የአንገት ሐብላቸውን አውልቀው ወሰዱባቸው፡፡ ከዚህም ሌላ የማስታወሻ ደብተራቸውን ጭምር ወሰዱባቸው፡፡
በማስታወሻቸው ላይ ከመያዛቸው ሦስት ቀን በፊት ለአቶ መንበረ 10ሺ ብር ሰጥተው ኖሮ፣ ያን የሰጡትን ገንዘብ በማስታወሻቸው ላይ ጽፈውት ስለተገኘ፣ አቶ መንበረን ከታሰሩበት ቦታ ሄደው ገንዘቡን ለምን እንደወሰዱ ጠይቀው፣ “ለልጆቼ ማሳደጊያ ነው” ሲሉ፤ “አምጡ” ተብለው ያንን 10ሺ ብር መልሰው ለደርጉ አስረከቡ፡፡ ጃንሆይ የገቡባት ክፍል አራት በሦስት ስፋት ያላት ክፍል ስትሆን በውስጧም የነበሩት ሁለት ጥቋቁር የቆዳ ወንበሮች ብቻ ነበሩ፡፡ ክፍሉንና ወንበሮቹን ራሴ አይቻለሁ፡፡ ያን ጊዜ ጊዜ የነበሩት ከበረንዳ ላይ ነበር፡፡ የልዕልት ተናኘወርቅም ቦርሳ እንደዚሁ ተይዞ ከውጭ ቀርቶአል፡፡ በ12 ሰዓት አልጋና ምንጣፍ ስለሄደ ሊነጠፍላቸው ሲል፤ “ምንም አልፈልግም” ብለው ምንጣፉን አስወጥተው ጣሉት፡፡ አልጋው ደግሞ ሁለት ፍራሽ ስለነበረው፣ የላይኛውን ፍራሽ አንሱ ብለው አስነስተው እታችኛው ላይ ተኙ፡፡ ብርድ ልብሳቸውም አንድ ብቻ እንዲሆን አድርገው ከዚያው አደሩ…
=====
“…እኛ እኮ እጃችንን የሰጠነው አውቀን ነው፡፡ ይህ ሁሉ እንደሚመጣ አስቀድመን የተረዳነው ጉዳይ ነው፡፡ እኛ በሰላም እጃችንን የሰጠነው የህዝቡ ደም እንደራሺያና ፈረንሳይ ሪቮሉሲዮን በከንቱ እንዳይፈስ በማሰብና መከራችንን እኛው እንቀበል በማለት ነው፡፡ የሩሲያንም ሆነ የፈረንሣይን ሪቮሉሲዮን ደህና አድርገን ስለምናውቅ ነው፡፡ ከዚህ በላይ የወታደሩ እንቅስቃሴ ሶሺያሊስት እንደሚሆን አስቀድመን ተገንዝበነዋል፡፡ ስለዚህ ከላይ ባሉት አገሮች የደረሰው እልቂት በእኛም አገር እንዳይደርስ በማሰብ ነው፡፡ ነገሩ ሁሉ ሲጀመር ይህ በቀጥታ እንደሚመጣ እናውቀው ነበር፡፡ እግዚአብሔር ያመጣው ስለሆነ መታገል አይቻልም፡፡ የወደፊቱንስ ማን ያውቃል፡፡ ሁሉ በእርሱ እጅ አይደል?”…