Administrator

Administrator

በሰአሊና ደራሲ ገዛኸኝ ዲኖ የተፃፈው “በቃ እንሂድ” የተሰኘ ልብወለድ መፅሀፍ የፊታችን ማክሰኞ በሩሲያ የሳይንስና የባህል አዳራሽ ከቀኑ 10፡00 ሰዓት ጀምሮ ይመረቃል፡፡ 460 ገፅ ያለውና መቼቱን ኢትዮጵያና ፈረንሳይ ላይ ያደረገው መፅሃፉ፤ በአንድ ሰዓሊ ህይወት ላይ ያጠነጥናል፡፡ በምርቃት ስነ-ስርዓቱ እለት ደራሲያንና ሌሎች እንግዶች የሚገኙ ሲሆን በመፅሀፉ ዙሪያ ውይይት ይካሄዳልም ተብሏል፡ መፅሐፉ በ70 ብር ከ85 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡ የመፅሃፉ፤ ደራሲ ሰዓሊ ገዛኸኝ ዲኖ ለ19 ዓመታት በፈረንሳይ አገር እንደኖረ ታውቋል፡፡

  •  ከትኬት ሽያጭ ቢያንስ 5 ሚሊዮን ብር እንደተገኘ ተገምቷል *
  • “ኮንሰርት” የሚወዱ “የእጅ አመለኞች” አስቸግረው ነበር

ከወራት በፊት ሊካሄድ ታቅዶ የነበረው “ሬጌ ዳንሶል ኢን ኢትዮጵያ ቁጥር 1” የሙዚቃ ኮንሰርት የተሰረዘው ከቴዲ አፍሮ ኮንሰርት ጋር በመገጣጠሙ እንደነበር አዘጋጁ “አውሮራ ኤቨንት ኦርጋናይዘርስ” መግለጹ ይታወሳል፡፡ የኮንሰርቱ ተጋባዥ ከያኒ ጃማይካዊው ቢዚ ሲግናል ለሸገር ሬዲዮ በሰጠው ቃለምልልስ ደግሞ፤ “ኮንሰርቱ የተሰረዘው በተለያዩ ምክንያቶች በተከሰቱ መዘግየቶች ነው” ብሎ ነበር፡፡ የሆነ ሆኖ “ለሁሉም ጊዜ አለው” እንዲሉ፣ ኮንሰርቱ ባለፈው ሳምንት ቅዳሜ በሚሊኒየም አዳራሽ በርካታ ታዳሚያን በተገኙበት ተካሂዷል፡፡ የምሽቱ ድባብ ከምሽቱ 2፡00 ላይ የተጀመረው የሙዚቃ ኮንሰርቱ፤ በአገራችን የሬጌ ሙዚቃ አቀንቃኞችና በዲጄ እየተሟሟቀ የዘለቀ ሲሆን ራስ ጃኒ፣ ሲዲኒ ሳልመን፣ ጃሉድ አወል፣ ሃይሌ ሩትስ እና ጆኒ ራጋ ማራኪ ሥራዎቻቸውን አቅርበዋል፡፡

በየመሃሉ በዲጄ ባባ ትንፋሽ እያገኙ መድረኩን ያደመቁት ኢትዮጵያዊ ድምፃዊያን፤ በታዳሚው ዘንድ ከፍተኛ አድናቆትን አግኝተዋል፡፡ መድረኩ በጥሩ ሁኔታ ተዘጋጅቷል፤ የላይትና የድምፁ ቅንብር እንከን የለሽ ነበር፡፡ ኮንሰርቱ ተጀምሮ እስከሚያልቅ አንድም የድምፅ መቆራረጥና መረበሽ አላጋጠመም፡፡ ድምፃዊያኑ ለኮንሰርቱ በቂ ዝግጅት ለማድረጋቸው በመድረክ ያሳዩት ጥንካሬና ብቃት ምስክር ነው፡፡ ራስ ጃኒ የምሽቱ ምርጥ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ጃሉድ “የገጠር ልጅ ነኝ”፣ “አሻበል ያሆ”፣ የእርግብ አሞራ እና ሌሎችንም ስራዎቹን በጥሩ ሁኔታ በመጫወት ታዳሚውን የማረከ ሲሆን ሃይሌ ሩትስ በበኩሉ፤ “ባዶ ነበር”፣ “እርጅና መጣና” በተሰኙ ታዋቂ ዘፈኖቹ ተመልካቹን አዝናንቷል፡፡ ጆኒ ራጋም አነቃቂ ምሽት ለመፍጠር ችሏል፡፡ ጆኒ ራጋና ሃይሌ ሩትስ በጋራ ተቀናጅተው ያቀረቡት ሥራም ልዩ አድናቆት የተቸረው ነበር፡፡ በየመሃሉ ዲጄ ባባ መድረኩን በሙዚቃ እያደመቀ፣ አርቲስቶቹም ትንፋሽ እየሰበሰቡ፣ ታዳሚውም ልቡ እስኪወልቅ እየጨፈረና እየዘለለ ጊዜው ወደ አምስት ሰዓት ነጐደ፡፡

የዕለቱ “ሰርፕራይዝ” መድረኩን በጥሩ ሁኔታ በመምራት የተሳካለት ጋዜጠኛ አንዷለም ተስፋዬ፤ በኮንሰርቱ መጀመሪያ ላይ “ሰርፕራይዝ” እንዳለ በመግለጽ የታዳሚውን ልብ አንጠልጥሎት ነበር፡፡ እናም የመድረኩ መብራት ደብዝዞ፤አይን የማያጨልም ድባብ ተፈጠረ፡፡ ሰፋፊ ኮፍያ ያደረጉ ሰዎች ደንገዝገዝ ባለው ድባብ ውስጥ እየሮጡ ወደ መድረኩ በመግባት ቦታ ቦታቸውን ያዙ፡፡ ታዳሚው ለ“ሰርፕራይዙ” ጓጉቶ ነበር፡፡ የመድረኩ መብራት ፏ ብሎ በራ፡፡ “ሰርፕራይዟ” ዘፋኝ፤ ነጭ ብልጭልጭ ቲ-ሸርትና ነጭ ቁምጣ ለብሳ ብቅ አለች፡፡ ጭብጨባና ፉጨቱ ቀለጠ፡፡ ድምጻዊት ቤቲ ጂ. “ከአንተ አይበልጥም” የሚለው ዘፈኗን በዳንስ ቡድኗ ታጅባ፣ አብራ እየተውረገረገች አስነካችው፡፡ እየዘፈነችና እየጨፈረች ታዳሚውን አስጨፈረችው፡፡ ሁለተኛ ዘፈኗም ቀጠለ፡፡ በጣም ግሩም አቀራረብ ነበር ያሳየችው፡፡ ሥራዋን ጨርሳ ከመድረክ ስትወርድም በህዝቡ አድናቆትና ሆታ ተሸኝታለች፡፡ የታዳሚውን ልብ የነካ ስራ “እኔ የፕሮግራሙ አዘጋጅ ሆኜ እንኳን አላወቅሁም፤ በጣም የተገረምኩበትና የተደነቅሁበት ጉዳይ ነው” ይላል፤የ“አውሮራ ኤቨንትስ ኦርጋናይዘርስ” ዋና ስራ አስኪያጅ ሸዊት ቢተው፡፡ ቤቲ ጂ.፣ ጃሉድ አወል፣ ሃይሌ ሩትስ እና አንድ ፊቱ አዲስ የሆነ አርቲስት ወደ መድረክ ወጡና ማንም ያልጠበቀውን ዘፈን መዝፈን ጀመሩ፡ “ነገን ላያት እጓጓለሁ” በማለት፡፡

ይሄን ጊዜ ታዳሚው መጮህ፣ ማልቀስና ማፏጨት ያዘ፡፡ በድንገተኛው ዘፈን አዳራሹ ተደበላለቀ፡፡ ከአመት በፊት በድንገት ህይወቱ ያለፈውን የሬጌውን አቀንቃኝ ድምፃዊ ኢዮብ መኮንን ለመዘከር ታስቦ የቀረበው ሙዚቃ የመላ ታዳሚውን ልብ የነካ ነበር፡፡ በመሃል “ወይኔ እዮቤ ውውው…” በማለት ጩኸቷን ያቀለጠችው አንዲት ወጣት ታዳሚ፤እንባዋ በጉንጯ እየወረደ ደረቷን መድቃት ጀመረች፡፡ ጓደኞቿ ተረጋጊ እያሉ ቢያፅናኗትም አልቻለችም፡፡ “እዮቤን በጣም ነው የማደንቀው፤ አሟሟቱም በጣም ያሳዝናል” እያለች ማልቀሷን ቀጠለች፡፡ የብዙሃኑ ታዳሚ ጩኸት፤ ፉጨትና ዝላይማ በቃላት ለመግለጽ አዳጋች ነው፡፡ “ነገን ላያት እጓጓለሁ” ቀጠለ፡፡ አርቲስቶቹ በጣም ያምሩ ነበር፤የሙያ አጋራቸውን የዘከሩበት መንገድም አንጀት ይበላል፡፡ “ይህንን ሃሳብ ያፈለቁት ዝግጅቱን ከእኛ ጋር በአጋርነት የሰሩት የሲግማ ኢንተርቴይንመንት የስራ ባልደረባ ብሩክ እና የአውሮራ ማኔጅመንት አባል ዳዊት ናቸው” ይላል ሸዊት፡፡

ያረፈደው የክብር እንግዳ እኩለ ሌሊት አለፈ፡፡ የእለቱ የክብር እንግዳ ብቅ አላለም፡፡ ዲጄ ባባ የመሸጋገሪያውን ሙዚቃ እያጫወተ 7፡45 ሆነ፡፡ የመድረኩ አጋፋሪ አንዷለም ተስፋዬ ብቅ አለ፡፡ “አሁን በጉጉት የምትጠብቁት እንቁ ድምፃዊ ቢዚ ሲግናል ወደ መድረክ ይመጣል” ሲል አዳራሹ በጩኸት ተሞላ፡፡ ከስንት ጥበቃ እና ጉጉት በኋላ ቢዚ ሲግናል ወደ መድረክ ሲመጣ አዳራሹ ይበልጥ ተናጋ፡፡ ዳልቻ ኮት በነጭ ሸሚዝና ጠቆር ባለ ግራጫ ሱሪ ያደረገው ቢዚ ሲግናል፤ ነጭ ፍሬም ያለው ጥቁር መነፅር ፊቱ ላይ ሰክቶ ለታዳሚው ሰላምታ ሰጠ፡፡ የእሱን ዘፈን ለመስማት ዝግጁ መሆን አለመሆናችንን ጠየቀ፤ “Are you feeling good?” (በጥሩ ስሜት ውስጥ ናችሁ እንደማለት) ታዳሚው በፉጨት እና በጭብጨባ ምላሽ ሰጠ፡፡ በዚህ ምሽት ከዚህ ውብ ህዝብ ጋር በመገናኘቱ የተሰማውን ደስታ አርቲስቱ ገለፀ፡፡ በግምት በ20ዎቹ አጋማሽ ዕድሜ ላይ የሚገኘው ቢዚ ሲግናል፤ እንደብዙዎቹ የሬጌ ሙዚቀኞች ፀጉሩ ድሬድ አይደለም፡፡

ምንም እንኳ በዘፋኝነት ይበልጥ የታወቀው “One more night” የተሰኘውን የፊል ኮሊንሰን ቀደምት ስራ ሪሚክስ አድርጎ ከተጫወተ በኋላ ቢሆንም በርካታ የራሱን ስራዎችም አበርክቷል፡፡ ቢዚ ሲግናል ወደ መድረክ የመጣው ታዳሚው በጭፈራ ጉልበቱን ከጨረሰ በኋላ ነበር፡፡ በየመሃሉ “ቢዩቲፉል ሌዲስ” እያለ ኢትዮጵያውያን ሴቶችን በማድነቅ ማቀንቀኑን ቀጠለ፡፡ አጠገቤ የነበሩ በቡድን የታደሙ ሰዎች “በቃ ያቺን ዋን ሞር ናይት ይዝፈናትና እንሂድ” ሲሉ ሰማኋቸው፡፡ እርሱ ግን አውቆም ይሁን ሳያውቅ ዘፈኗን ወደ መጨረሻ ላይ አደረጋት፡፡ ሲግናል እስከ ሌሊቱ 9፡41 ድረስ መድረክ ላይ ነበር፡፡ ታዳሚው ግን ከቢዚ ሲግናል ይልቅ በኢትዮጵያዊያን አርቲስቶች ይበልጥ መደሰቱን ታዝቤአለሁ፡፡ የኮንሰርቱ አንዳንድ እንከኖች በምሽቱ ድራፍትና ሃሺሽ እኩል ሲጠጡ አመሹ ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ ሀሺሽ በየደቂቃውና በየቅርብ ርቀቱ ይጨሳል፤ እንደጉድ ይጦዛል፡፡ ለሽታው ባዕድ የሆነ ያጥወለውለዋል፡፡ ያስመለሳቸውም ነበሩ፡፡ አጠገቤ የነበረ አንድ ታዋቂ አርቲስት፣ ሃሺሽ ከሚያጨስ አንድ ወጣት ጋር አንገት ለአንገት ሲተናነቅ አይቻለሁ- “ሌላ ቦታ ሄደህ አጭስ” በሚል፡፡ በርካታ ኪስ አውላቂዎችም (ሌቦች) አሰላለፋቸውን አሳምረው ነበር፡፡

ቦርሳዎች፣ ሞባይል ስልኮች፣ የኪስ ቦርሳዎችና ሌሎች ንብረቶች ለመንታፊዎች ሲሳይ ሆነው አምሽተዋል፡፡ አንድ የውጭ ዜጋ “ዋሌቴን ተሰርቄአለሁ፤ ውስጡ ፓስፖርት አለው፤ እባካችሁ እዚሁ እንዳልቀር ፓስፖርቱን እንኳን መልሱልኝ” የሚል መልዕክት በመድረክ አጋፋሪው አስነግሯል፡፡ ባለረጃጅም ተረከዝ ጫማዎችን የተጫሙ ሴቶች እግራቸውን ሲደክማቸው ጫማቸውንና ቦርሳቸውን መሬት ቁጭ አድርገው ሲጨፍሩ የሌባ ሰለባ ሆነዋል፡፡ አንዲት ወጣት “ሌላው ቢቀር ጫማዬን እንኳን ባገኝ---” በማለት እንባዋ እንደጎርፍ እየፈሰሰ፣በታዳሚው ስር በመሽሎክሎክ ጫማዋን ስትፈልግ አስተውያለሁ፡፡ የ“አውሮራ ኤቨንትስ ኦርጋናይዘርስ” ዋና ሥራ አስኪያጅ ሸዊት ቢተው ስለስርቆቱ ጠይቀነው ሲመልስ፤ “የእኛ ኮንሰርት የመጀመሪያ ከማይመስልባቸውና ከሚለይባቸው ጉዳዮች መካከል በምሽቱ ከካራማራ ፖሊስ ጋር በመተባበር አዳራሽ ውስጥ ሆነው የሰው ንብረት የሰረቁ ሌቦችን ይዘን ሞባይል፣ ቦርሳ፣ ፓስፖርትና ሌሎች ንብረቶችን ለባለቤቶቹ ማስመለሳችን ነው” ብሏል፡፡ ከተሰረቁት እቃዎች አብዛኞቹ ለባለቤቶቹ እንደተመለሱና አንድ ሁለት ሰዎች ብቻ እቃቸውን ማግኘት እንዳልቻሉ ሸዊት ተናግሯል፡፡ ኮንሰርቱን ከ10 እስከ 12ሺህ የሚደርሱ ሰዎች እንደታደሙት ከዚህም ውስጥ 2ሺህ ያህሉ በተጋባዥነት እንደገቡ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከትኬት ገቢም ቢያንስ 5 ሚሊዮን ብር ገደማ እንደተገኘ ተገምቷል፡፡

ክሪስ ፕሩቲ ስለ ዳግማዊ አፄ ምኒልክ እና እቴጌ ጣይቱ የፃፈችውን መፅሀፍ፣ ውብሸት ስጦታው (ክፉንድላ) ወደ አማርኛ በመመለስ “ዳግማዊ ምኒልክና እቴጌ ጣይቱ” በሚል ርዕስ አሳትሞ ሰሞኑን ለገበያ አውሏል፡፡ መፅሀፉ ስለኢትዮጵያዊያን ስም አወጣጥ፣ የጣይቱ 5ኛ ባል ስለሆኑት የሸዋው ንጉስ አፄ ምኒልክ፣ ስለጣይቱ የእቴጌነት ማዕረግ፣ ከጣልያን ጋር ስለተደረጉት የአምባላጌ፣ የመቀሌና የዓድዋ ጦርነቶችና በርካታ ተያያዥ ታሪኮች ተካተውበታል፡፡ በ18 ምዕራፍ ተከፋፍሎ በ459 ገፅ የተመጠነው መፅሀፉ፤ በ80 ብር ለገበያ የቀረበ ሲሆን ባሳለፍነው ሳምንት ደራሲያን፣ ሃያሲያንና ጋዜጠኞች በተገኙበት በእቴጌ ጣይቱ ሆቴል ተመርቋል፡፡

እናት ልጃቸው ያለቅጥ ማምሸቱ አስግቷቸዋል፡፡ ይወጣሉ ይወርዳሉ፡፡ የ26 ዓመት ልጃቸው መጠጥ አይቀምስም፣ ብዙ ጓደኞችም የሉትም፡፡ ሁሌም በጊዜ ወደቤቱ የመግባት ዓመል ነበረው፤ዛሬ ግን የበላው ጅብ አልጮህ አለ፡፡ (የዛሬ 2 ዓመት ገደማ ነው) እናት ወገባቸውን በነጠላቸው አስረው እያቃሰቱ፣ ወደ አራዳ ክ/ከተማ ፖሊስ በመሄድ፣ ልጃቸው እንደጠፋባቸውና የሞባይል ስልኩም እንደማይሰራ እንባ በጉንጫቸው እየፈሰሰ ለፖሊስ ተናገሩ፡፡ ስሙንና መልኩንም በደንብ አብራሩ፡፡
ፖሊስ ይሄኔ የልጁ ማንነት ገባው፡፡ ወጣቱ የመኪና አደጋ ደርሶበት፣ ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል ድንገተኛ ክፍል ገብቶ፣ ሃኪሞች አስቸኳይ የሲቲስካን ምርመራ እንዲያደርግና ውጤቱን ፖሊሶች ይዘው እንዲመጡ አዘው ነበር፡፡ ፖሊሶችም አደጋው የደረሰበትን ወጣት፣ ወደ “ውዳሴ ዲያግኖስቲክ የምርመራ ማዕከል” በመውሰድ ምርመራው በነፃ እንዲያገኝ አደረጉ
ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የአራዳ ክ/ከተማ ትራፊክ ጽ/ቤት የሥራ ኃላፊ ስለውዳሴ ዲያግኖስቲክ በሰጡት አስተያየት፤ “ምንም እንኳን ወጣቱ በደረሰበት ከባድ የመኪና አደጋ ከሞት ባይተርፍም ማዕከሉ ግን አስቸኳይ ምላሽ ሰጥቶት ነበር፤ ከእኛ ጋር በመተባበር በሚሰሩት ስራ ከፍተኛ አድናቆት አለን” ብለዋል፡፡
እንደዚህ መሰል አደጋዎች፣ አሊያም በተፈጥሮ በህመም ምክንያት በሃኪም የሲቲስካን ምርመራ ሲታዘዝ ዋጋው ከሌሎች ምርመራዎች ስለሚወደድ ብዙ ሰዎች እድሉን ሳያገኙ ለህልፈት ይዳረጋሉ፡፡ በዚህ ረገድ ያለውን የሰዎች ችግር ለመቅረፍ የሚሰራው “ውዳሴ ዲያግኖስቲክ የምርመራ ማዕከል”፤ ዘንድሮ ለአራተኛ ጊዜ “ጳጉሜን ለጤና” በሚል መርህ፤ ከ500 በላይ ለሆኑ ሰዎች ነፃ የሲቲስካን ምርመራ እንደሚያደርግ የማዕከሉ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዳዊት ሃይሉ አስታወቁ፡፡ ማዕከሉ በ2001 ዓ.ም ተቋቁሞ 65 ያህል ሰራተኞችን እንደሚያስተዳድር የገለፁት ስራ አስኪያጁ፤ ባለፉት ሶስት ዓመታት መርህ ከ5ሺህ በላይ ለሆኑ የሲቲስካን ምርመራ ፈላጊዎችና በራሳቸው ለመመርመር አቅም ለሌላቸው ሰዎች አገልግሎቱን እንደሰጠ አብራርተዋል፡፡
“አንድ ለትርፍ የተቋቋመ ድርጅት ከሚያገኘው ነገር ላይ አቅም የሌላቸውን መርዳትና ማህበራዊ ኃላፊነቱን መወጣት አለበት” ያሉት አቶ ዳዊት፤ በየአመቱ በጳጉሜ ወር በዘመቻ መልክ ነፃ የምርመራ አገልግሎት እንደሚሰጡ ተናግረዋል፡፡ የማዕከሉ የማርኬቲንግ እና የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ወ/ሮ ሰብለ ኃይሉ እንደገለፁት፤ ከአራዳ ክ/ከተማ ትራፊክ ፅ/ቤት ጋር በመተባበር የመኪና አደጋ ደርሶባቸው የሲቲስካን ምርመራ ለሚስፈልጋቸው ሰዎች፣ በየትኛውም ሰዓትና ቀን ነፃ የምርመራ አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ “ዓመቱን ሙሉ ቢያንስ ከ4-5 ሰው በየቀኑ በተለያየ ምክንያት ምርመራው አስፈልጎት ሲመጣ ነፃ ምርመራ ያገኛል” ያሉት ወ/ሮ ሰብለ፤ ጳጉሜ ላይ በዘመቻ መልክ ለብዙ ሰዎች አገልግሎቱን የምንሰጠው ሌላውም ኃላፊነቱን እንዲወጣ ምሳሌ ለመሆን ነው ብለዋል፡፡
“ምንም እንኳ ለትርፍ የተቋቋምን ብንሆንም መልካም ስራ ኪሳራ የለውም” ያሉት ወ/ሮ ሰብለ፤ ሰውን ማትረፍ መቻል በራሱ ትርፍ ነው ብለዋል፡፡ ማዕከሉ ባለፈው ዓመት ጳጉሜ ለ500 ሰዎች ነፃ ምርመራ ለማድረግ ጥሪ አቅርቦ፣ 950 ሰዎች መመዝገባቸውንና ሁሉም ነፃ ምርመራውን እንዳገኙ ተናግረዋል፡፡ የማዕከሉ ዋና ስራ አስፈፃሚ ቃለክርስቶስ ሃይሉ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫም፤ ማንኛውም የአገልግሎቱ ፈላጊ የሚመለከተው የመንግስት አካል በግሉ ለመርመር እንደማይችል ጠቅሶ ደብዳቤ ከፃፈለትና ሃኪም ምርመራው ያስፈልገዋል ብሎ ከመሰከረ፣ 500 ቢባልም የመጣው ሁሉ መመርመሩ አይቀርም ብለዋል፡፡
“ውዳሴ ዲያግኖስቲክ” በዚህ የበጎ አድራጎትና ማህበራዊ ኃላፊነትን የመወጣት እንቅስቃሴው እንደሚቀጥል የገለፁት ስራ አስኪያጁ፤ ማዕከሉ በሚገኝበት አራዳ ክ/ከተማ  ነዋሪ ለሆኑ ታካሚዎች 20 በመቶ የክፍያ ቅናሽ እንደሚደረግላቸው ተናግረዋል፡፡ ማዕከሉ ከዚህም በተጨማሪ ለክ/ከተማው ነፃ የአምቡላንስ አገልግሎት ይሰጣልም ተብሏል፡፡
ለነፃ ምርመራ ጳጉሜን ለምን መረጣችሁ በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ አቶ ዳዊት ሲመልሱ፤ “ጳጉሜ አሮጌው አመት አልቆ ወደ አዲስ አመት መሸጋገሪያ እንደመሆኑ መጠን፣ ሰዎች ነፃ ምርመራ አግኝተው በተስፋና በደስታ አዲሱን ዓመት እንዲቀበሉ የበኩላችንን ለማድረግ አስበን ነው” ብለዋል፡፡

ቀይ ስጋ፣ ስብና ጨው የበዛባቸው ምግቦች አይበረታቱም  

በሳምንት ከ10 ፖርሽን (1 ፖርሽን ለአንድ ሰው የሚበቃ ምግብ መጠን ነው) በላይ ቲማቲሞችን የሚመገቡ ወንዶች በዘር ፍሬ ዕጢዎች ካንሰር (Prostate Cancer) የመያዝ አደጋን 20 በመቶ እንደሚቀንሱ በእንግሊዝ የተደረገ ጥናት ጠቆመ፡፡
የብሪስቶል ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ቡድን 20ሺህ የሚደርሱ ዕድሜያቸው ከ50-69 ዓመት የሆኑ የእንግሊዝ ወንዶችን የአመጋገብና የአኗኗር ዘዬ ያጠና ሲሆን, በየሳምንቱ ከ10 ፖርሽን በላይ ቲማቲሞችን (የተቆረጡ ቲማቲሞች፣ የቲማቲም ጭማቂ፣ በቲማቲም ሱጎ የተጋገረ ባቄላ) የተመገቡ ወንዶች በዘር ፍሬ እጢ ካንሰር የመጠቃት ዕድላቸው 18 በመቶ መቀነሱን ተመልክቷል፡፡
“የጥናት ውጤታችን ቲማቲም የዘር ፍሬ እጢ ካንሰርን በመከላከል ረገድ ጠቃሚ እንደሆነ ይጠቁማል” ያሉት ብሪስቶል ዩኒቨርሲቲ የህክምና ት/ቤት ተወካይ ቫኔላ ኢር፤ ግኝታችንን ለማረጋገጥ ተጨማሪ ጥናቶች መካሄድ አለባቸው ብለዋል፡፡
“ወንዶች በርካታ የተለየዩ ዓይነቶች አትክልቶችና ፍራፍሬዎችን መመገብ፣ ጤናማ የሰውነት ክብደታቸውን መጠበቅና አካላዊ እንቅስቃሴ ማድረግ አለባቸው” ሲሉ መክረዋል ቫኔላ፡፡
ተመራማሪዎቹ የዘር ፍሬ እጢዎች ካንሰርን የሚከላከሉ ሌሎች ሁለት የምግብ ዓይነቶችንም መርምረዋል፡፡ ዳቦና ፓስታ በመሳሰሉት ከዱቄት የሚዘጋጁ ምግቦች ውስጥ የሚገኘው ሴሊኒየም የተባለ ንጥረ ነገር እንዲሁም ወተትና ቺዝ በመሳሰሉት የወተት ውጤቶች ውስጥ የሚገኘው ካልሲየም በፕሮስቴት ካንሰር የመጠቃት አደጋን እንደሚቀንሱ ተመራማሪዎቹ ጠቁመዋል፡፡ ቲማቲምንና ከላይ የተጠቀሱትን ሁለት የምግብ ንጥረ ነገሮች በቅጡ የሚጠቀሙ ወንዶች ለበሽታው የመጋለጥ ዕድላቸው ዝቅተኛ ነው ብለዋል አጥኚዎቹ፡፡
በጥናቱ ላይ አስተያየት የሰጡት ዶ/ር አያይን ፍሬም በፕሮስቴት ካንሰር የመያዝ አደጋን ለመቀነስ ይችሉ ዘንድ ወንዶች የትኞቹን የተወሰኑ ምግቦች መብላት እንዳለባቸው ተጨባጭ ጥቆማ ለመስጠት የሚያስችል በቂ ማስረጃ አልተገኘም ብለዋል፡፡
ወንዶች እንደ ቲማቲማ ባለ አንድ የምግብ ዓይነት ላይ ብቻ መተማመን የለባቸውም የሚሉት ዶ/ር ፍሬም፤ “ጤናማ፣ በዛ ያሉ አትክልትና ፍራፍሬዎችን ያካተተ የተመጣጠነ ምግብ ከመደበኛ የአካል እንቅስቃሴ ጋር ይበልጥ የተሻለ አማራጭ ነው” በማለት አስረድተዋል - ዶ/ር ፍሬም፡፡
የዩኬ ካንሰር ምርምር ተቋም ተወካይ ቶም ስታንስፌልድ በበኩላቸው፤ “ላይኮፒኒ በተባሉ ንጥረነገሮች የበለፀጉ እንደቲማቲም ያሉ ወይም ሴሌኒየም የያዙ ምግቦች የፕሮቴስት ካንሰር አደጋን ከመቀነስ ጋር ሊያያዙ ይችላሉ፤ ነገር ግን ይሄ ነገር አልተረጋገጠም፤ የአሁኑ ጥናት በምግብና በፕሮስቴት ካንሰር መካከል ግንኙነት ይኑር አይኑር ሊያረጋግጥ አይችልም” ብለዋል፡፡
ነገር ግን ሁሉም ወንዶች የፍራፍሬና አትክልት ይዘቱ ከፍተኛ የሆነ የተመጣጠነ ምግን እንዲያዘወትሩ እናበረታታለን ያሉት ቶም ስታንስፌልድ፤ ቀይና በፋብሪካ የተቀነባበረ ስጋ እንዲሁም ስብና ጨው የበዛባቸው ምግቦችን በእጅጉ መቀነስ እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡
የዘር ፍሬ እጢዎች ካንሰር በመላው ዓለም በወንዶች ላይ በስፋት የተሰራጨ ሁለተኛው የካንሰር ዓይነት ሲሆን በእንግሊዝ በየዓመቱ 10ሺ ገደማ ወንዶች በበሽታው ይሞታሉ፡፡ 

Saturday, 30 August 2014 10:57

የጸሐፍት ጥግ

ጉድጓድ ውስጥ ስትሆን መቆፈርህን አቁም፡፡
       ዴኒስ ሂሌይ (እንግሊዛዊ የፖለቲካ መሪ)
በርቀት ያለ ውሃ በአቅራቢያ የተነሳ እሳትን አያጠፉም፡፡
ሃን ፌይ (ቻይናዊ ፈላስፋ)
ካልተሰበረ አትጠግነው፡፡
 ቤርት ላንስ (አሜሪካዊ ባለሥልጣን)
ከምናውቀው የበለጠ ብልህ ነን፡፡
ራልፍ ዋልዶ ኤመርሰን
(አሜሪካዊ ገጣሚና ወግ ፀሐፊ)
ቡትቶ ለብሰህ ተደራድረህ ሃር ልትለብስ ትችላለህ፡፡
የአይሁዶች አባባል
ታዳጊ የቀርከሃ ዛፎች በቀላሉ ይጎብጣሉ፡፡
የቬትናሞች አባባል
ጎረቤትህን እባብ ከነደፈው አንተም አደጋ ላይ ነህ፡፡
የአፍሪካዊያን (ስዋሂሊ) አባባል
እውነተኛ ወርቅ እሳት አይፈራም፡፡
የቻይናዊያን አባባል
ሚስት የሌለው ወንድ ልጓም እንደሌለው ፈረስ ነው፡፡
የቬትናሞች አባባል
ኮረዳ ወላጆቿን ለማስደሰት ስታገባ፣ ባሏ የሞተባት ራሷን ለማስደሰት ታገባለች፡፡
የቻይናዊያን አባባል
ልብ ውስጥ የተፃፈ ደብዳቤ ፊት ላይ ይነበባል፡፡
የአፍሪካዊያን (ስዋሂሊ) አባባል

ሜሪ ጄን ዋግል ትባላለች፡፡ አሜሪካዊት ናት፡፡ በሙያዋ የከተማ ፕላን አውጪ (Urban planner) ብትሆንም በ2013 ዓ.ም ወደ ኢትዮጵያ መጥታ ላለፉት ሶስት ዓመታት ገደማ የስኬታማ ኢትዮጵያዊያን ሴቶችን ታሪክ የሚዘክር መፅሃፍ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ስታዘጋጅ ቆይታለች፡፡ በመጪው መስከረም ወር መጨረሻ ላይ በእንግሊዝኛና በአማርኛ ቋንቋ የተዘጋጁት የ64 ስኬታማ ሴቶችን ታሪክ የያዙ መፅሀፍት ለንባብ የሚበቁ ሲሆን መፃሕፍቱ  ታዳጊ ሴቶች ላይ አተኩረው ለሚሰሩ የስልጠና ማዕከላትና ት/ቤቶች በነፃ ይሰራጫል ተብሏል፡፡ የአዲስ አድማስ ከፍተኛ ሪፖርተር አለማየሁ አንበሴ “ተምሳፀለት  የተሰኘው መፅሃፍ ጠንሳሽና አዘጋጅ ከሆነችው ሜሪ - ጄን ዋግል ጋር በመፅሃፉ ዙሪያ ያደረገው ቃለምልልስ እንዲህ ቀርቧል፡፡

          የስኬታማ ኢትዮጵያዊያን ሴቶችን አጭር የህይወት ታሪክ የሚዘግብ መፅሀፍ ማዘጋጀትሽን ሰምቻለሁ፡፡ መፅሃፉን ለማዘጋጀት ምን አነሳሳሽ? እስቲ ስለመፅሃፉ ጠቅለል አድርገሽ ንገሪኝ…
ወደ ኢትዮጵያ የመጣሁት እ.ኤ.አ በ2011 ዓ.ም ነው፡፡ አመጣጤም ከትውልድ ሃገሬ ውጪ ያሉኝን ልምዶች ለማካበት ነበር፡፡ በአጋጣሚ የኢትዮጵያ ሴቶች ማህበራት ጥምረት ፕሬዚዳንት ከሆኑት ወ/ሮ ሳባ ገ/መድህን ጋር የሃገሪቱ ሴቶች ላይ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተፃፉ መፅሃፎችን ማፈላለግ ጀመርኩ፡፡ ነገር ግን እንዳሰብኩት ላገኝ አልቻልኩም፡፡ በወ/ሮ መአዛ አሸናፊ የተፃፈው የሴቶች ፖለቲካዊ ተሳትፎን የሚተርክ መፅሃፍ ብቻ ነው ላገኝ የቻልኩት፡፡ ከዚህ ቀደም በሌሎች የአፍሪካ ሃገሮች በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተፃፉ የታላላቅ ሴቶችን ታሪክ አግኝቻለሁ፡፡ የኢትዮጵያዊያንን ስኬታማ ሴቶች የሚዘክር መፅሃፍ ግን ላገኝ አልቻልኩም፡፡ ይህን መነሻ በማድረግ በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተደራጀ መፅሃፍ ማዘጋጀት ቢቻል፣ የሃገሪቱ ታዳጊ ወጣት ሴቶች የቀደሙትን ሴቶች ታሪክና ልምድ እንዲሁም ጥንካሬ በሚገባ ተረድተው እንዲያድጉ ማድረግ ይቻላል በሚል መፅሃፉን ለማዘጋጀት ወሰንኩ፡፡ በዚህ ጉዳይ ላይ ወ/ሮ ሳባን ሳማክራት በጣም ተደሰተች፡፡ መፅሃፉ ጠቃሚ ነው ቀጥይበት አለችኝ፡፡
በዚህ መልኩ ስለውጤታማ ሴቶች መረጃዎች ማሰባሰብ ጀመርኩ፡፡ አብዛኞቹ ታሪኮች በጋዜጣና በመፅሄቶች ተበታትነው የሚገኙ ከመሆናቸውም በላይ ያልተሟሉ ናቸው፡፡ የተወሰኑ የአዲስ አበባ የሁለተኛ ዲግሪ ተማሪዎችን መርጠን መረጃዎችን በመፈለግ እንዲረዱን ጠየቅን፡፡ እነሱም ትብብራቸውን አልነፈጉንም፡፡ የታሪኩ ባለቤቶችና ቤተሰቦቻቸውን አፈላልጎ በማግኘት፣ ቃለመጠይቆችን ማድረግ፣ በእነሱ ዙሪያ የተፃፉትን ዘገባዎች ማሰባሰብና ሌሎችንም የስራው ሂደቶች አብረን ተወጥተናል፡፡ ሁሉም ሲያገለግሉ የነበረው በበጎ ፈቃደኝነት ነበር፡፡
በዝግጅቱ ወቅት ቃለመጠይቅ የተደረገላቸው ባለታሪኮች ራሳቸው ቃለ መጠይቃቸውን በራሳቸው ቋንቋ አርመው እንዲመልሱልን አድርገናል፡፡ ከ300 በላይ ሴቶች ነበሩ የተመረጡት፤  ከዚያ ውስጥ ነው ወደ 64 የሚሆኑት ተመርጠው በመፅሃፉ የተካተቱት፤ ነገር ግን የሁሉም ታሪክ ለታዳጊ ሴቶች የሚያጋራው የራሱ ነገር አለው፡፡ ለዚህ ሲባል በድረገፃችን ላይ የሁሉንም ሴቶች ታሪክ አስፍረናል፡፡
ፎቶግራፎችን በተመለከተም ታዋቂዋ ፎቶግራፍ አይዳ ሙሉነህ እንድታነሳ አድርገናል፡፡ ለሁለት አመት ገደማ የእነዚህን ባለታሪኮች ፎቶግራፍ ስታሰባስብና በስራ ላይ እያሉ ስታነሳ ቆይታለች፡፡ ፎቶግራፎቹ አለማቀፍ ደረጃቸውን የጠበቁና ጥራት ያላቸው ናቸው፡፡ የታተመውም በአሜሪካን ሃገር ሎሳንጀለስ በሚገኘው ፀሃይ ፕሬስ ማተሚያ ቤት ነው፡፡
በመፅሃፉ የተካተቱት ባለታሪኮች እንዴት ነው የተመረጡት?
በመፅሃፉ የተካተቱ ባለታሪኮችን ስንመርጥ ከፍተኛ ጥንቃቄ አድርገናል፡፡ ሴቶቹ ከተለያዩ የስራ ዘርፎች የተመረጡ ናቸው፡፡ ገበሬ ከሆኑት ጀምሮ የህዝብ መሪ እስከሆኑት ሴቶች ድረስ በጥልቀት ለመዳሰስ ተሞክሯል፡፡ የመጀመሪያዋ አውሮፕላን አብራሪ ሴት፣ የኮንስትራክሽን ክሬን ባለሙያ፣ አርቲስት፣ ሃኪም አምባሳደር… የመሳሰሉት በመፅሀፉ ተካተዋል፡፡ ከተለያዩ የሙያ ዘርፎች ለመምረጥ ተችሏል፣ ከኪነ- ጥበብ፣ ከማህበራዊ እንቅስቃሴዎች፣ ከህዝብና የመንግስት ሰራተኞች፣ ከመገናኛ ብዙሃን፣ በቢዝነስ ስኬታማ ከሆኑት፣ ከህክምና ሌሎችም የተመረጡ ናቸው፡፡ ከተለያዩ የሃገሪቱ ክፍሎች የተውጣጡ እንዲሆኑም ጥረት ተደርጓል፡፡ 64 ሴቶችን ብቻ ስንመርጥ በሃገሪቱ ስኬታማ እነዚህ ብቻ ናቸው ማለታችን አይደለም፡፡ የግዴታ መምረጥ ስላለብንና ማሳያ ይሆናሉ ብለን ስላሰብን እንጂ፡፡ የ300ዎቹን ሴቶች ታሪክ በሙሉ በመፅሃፉ ባናካትትም ድረገፃችን ላይ ታሪካቸው እንዲቀመጥ አድርገናል፡፡ ለወደፊት ታሪካቸው  በሌላ መፅሃፍ ታትሞ ሊወጣ ይችል ይሆናል፡፡ የ64 ሴቶች ታሪክ የያዘው ይህ አዲስ መፅሀፍ ግን የአዲስ ዓመት ስጦታ ይሆናል፡፡
የመፅሃፉ ፋይዳ ምንድን ነው? የትኛውን የህብረተሰብ ክፍልስ ያለመ ነው?
መጀመሪያ መፅሀፉ ታሳቢ የሚያደርገው ታዳጊ ሴቶችን ነው፡፡ እነዚህ ታዳጊዎች ለወደፊት የህይወት አቅጣጫቸውን ለመወሰንና በጥንካሬ ለመጓዝ ባለታሪኮቹ ምሳሌ ይሆኗቸዋል፡፡ ብዙውን ጊዜ የሚታሰበው ሴቶች ትምህርት ተማሩም አልተማሩም የሆነ እድሜ ላይ ሲደርሱ ባል ማግባት እንዳለባቸው ብቻ ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ወይ የቤት እመቤት ይሆናሉ አሊያም ባሎቻቸውን በስራ የማገዝ ኃላፊነት ይሸከማሉ፡፡ ትልቅ ደረጃ ስለመድረስ አይታሰባቸውም፡፡ ነገር ግን የእነዚህ ሴቶች የህይወት ተሞክሮ ስኬታማ መሆን እንደሚቻል ለታዳጊዎች በሚገባ ያስተምራል፡፡ ማድረግ የሚፈልጉትን ለማድረግ ምንም የሚሳናቸው ነገር እንደሌለ የባለታሪኮቹ ታሪክ ለታዳጊዎቹ ያሳያል፡፡
በመፅሀፉ ዝግጅት ወቅት ፈታኝ የነበሩ ሁኔታዎች ምንድን ናቸው?
አንዱ ትልቁ ፈተና የነበረው ሴቶቹን ማግኘት ነው፡፡ አንዳንዶቹ ታሪካቸውን ለመናገር አይደፍሩም፤ እንደውም የአንዷን ሴት ታሪክ ለማግኘት 3 ጊዜ ያህል መመላለስ ግድ ሆኖብን ነበር፡፡ የኢንተርኔት፣ የስልክ ችግሮችም ነበሩ፡፡ ሴቶቹን እንደልብ ማግኘት አንችልም ነበር፡፡ ታሪኮቹን ማረምም የራሱን ሰፊ ጊዜ ወስዷል፡፡ በመፅሃፉ ዝግጅት ላይ የተሳተፉትን ሰዎች ጊዜ ከተገቢው በላይ የተሻማ መፅሀፍ ነው፡፡ የተሰባሰቡትን መረጃዎች በፅሁፍ፣ በፎቶግራፍ፣ በዲዛይን ማቀናበር በራሱ አስቸጋሪና ጊዜ የወሰደ ነበር፡፡ ነገር ግን በበጎ ፈቃደኝነት የተሳተፉ ተማሪዎችን ጨምሮ የፎቶግራፍ እና ዲዛይን ስራውን የከወኑት ባለሙያዎች ለስራቸው ታማኝ በመሆናቸው ውጤታማ መሆን ተችሏል፡፡
መፅሃፉን ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ  መተርጎም በራሱ ከባድ ነበር፡፡ የትርጉም ስራውን የሰራው ኢዮብ ካሣ እና የፊደል ለቀማ (Proof readeing) የሰሩት ሰዎች እጅግ የሚደንቅ ስራ ሰርተዋል፡፡ ከእነዚህ ሰዎች ጋር በመስራቴ ኩራት ይሰማኛል፡፡
የገንዘብ ድጋፍ ያደረገው ማን ነው?
በአብዛኛው የመፅሃፉ ዝግጅት የተሰራው በበጎ ፍቃደኞች እገዛ ነው፡፡ መፅሃፉ ለንባብ ሲበቃ ለሁለተኛ ደረጃ ት/ቤቶች፣ ለቴክኒክና ሙያ ማሰልጠኛዎችና ለመሳሰሉት የትምህርት ተቋማት በነጻ ነው የሚሰራጨው፡፡ በመፅሃፉ ዝግጅት ወቅት 13 ያህል ተቋማት ትብብር አድርገውልናል፤ ድጋፋቸውንም ቸረውናል፡፡ የስዊድን መንግስት፣ ኮካኮላ ኩባንያ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሴቶች ጉዳይ፣ የእንግሊዝ አለማቀፍ የልማት ተቋም (DFIO)፣ የአውሮፓ ህብረት፣ የፈረንሳይ ኤምባሲ፣ የአሜሪካ ኤምባሲ፣ አይፓስ ኢትዮጵያ፣ ዴቪዲና ሉሲ አለማቀፍ ፋውንዴሽን፣ ፓዌ ኢትዮጵያ፣ አይርሽ ኤይድ የተለያዩ ድጋፎችን አድርገውልናል፡፡ መፅሀፉ ታዳጊ ሴቶችን በተለያዩ ሙያዎች ለሚያሰለጥኑ የትምህርት ተቋማት በነፃ እንዲበረከት የእነዚህ ተቋማት ድጋፍ ወሳኝ ሚና አለው፡፡
መፅሀፉ መቼ ነው አንባቢያን እጅ የሚደርሰው?
የመጀመሪያው የመፅሃፉ ህትመት ለሽያጭ አይቀርብም፡፡ እንዳልኩህ በነፃ ነው የሚታደለው፡፡ በቀጣይ የኢትዮጵያ ሴቶች ማህበራት ጥምረት የእንግሊዝኛና የአማርኛ ትርጉም መፅሃፉን ይፋ ሲያደርግ ምናልባት ለሽያጭ ሊቀርብ ይችላል፡፡ የዚህ መፅሃፍ ምረቃ የሚካሄደው መስከረም 27 ቀን 2007 ዓ.ም ነው፡፡ የምረቃ ቦታውም በብሄራዊ ሙዚየም ይሆናል፡፡ የፎቶግራፍ ባለሙያዋ አይዳ ሙሉነህ ያነሳቻቸው ፎቶዎችም በኤግዚቢሽን መልክ ይቀርባሉ፡፡ በሌሎች ሃገሮች ተመሳሳይ ፕሮጀክቶች ላይ ሰርተሽ ታውቂያለሽ?
አይ! በሌላ ሃገር እንዲህ አይነት ስራ ላይ ተሳትፌ አላውቅም፡፡ በሙያዬ የከተማ ፕላን አውጭ ነኝ፡፡ በአሜሪካ በቤቶች ልማት ላይ  ሰርቻለሁ፡፡ በመፅሃፍ ዝግጅት ደረጃ የአሁኑ የመጀመሪያዬ ነው፡፡
በኢትዮጵያ የነበረሽን ቆይታ እንዴት ትገልጭዋለሽ?
ኢትዮጵያን በጣም ወድጃታለሁ፡፡ አስደናቂና ውብ ሃገር ነች፡፡ ባህሉ ጥልቅ ነው፣ በቤተሰብና በሃይማኖት ዙሪያ ማዕከል ያደረገ ትስስሮሽና ባህል አላችሁ፡፡ ሰው አሜሪካ በበጎ ፍቃደኝነት አገልግሎት የተሻለች ናት ሲል እሰማለሁ፤ እኔ ግን እዚህም የበጎ ፍቃደኝነት አገልግሎት ለመስጠት ከፍተኛ ቁርጠኝነት እንዳለ በሚገባ አይቻለሁ፡፡ የሃገሬውን ምግቦችም ወድጃቸዋለሁ፤ ሽሮ ወጥ በጣም ነው የምወደው፡፡ ማኪያቶው ደግሞ የትም ሃገር የማይገኝ ልዩ ጣዕም ያለው ነው፡፡
ቀጣይ እቅድሽ ምንድን ነው?
መፅሀፉ ከተመረቀ በኋላ ወደ አሜሪካ እመለሳለሁ፡፡ መኖሪያ ቤቴ ሎስ አንጀለስ ነው፡፡ በሎስ አንጀለስ መደበኛ ስራዬን እቀጥላለሁ ብዬ አስባለሁ፡፡ በኢትዮጵያ የሰራሁትን ፕሮጀክት እዚያም ለመስራት እቅድ አለኝ፡፡
ስለቤተሰብሽ ሁኔታ ልትነግሪኝ ትችያለሽ?
አግብቼ ሶስት ልጆች ወልጄ ፈትቻለሁ፡፡ ሶስት ቆንጆ ሴት ልጆች አሉኝ፡፡ ሁሉም በተለያየ ቦታ ነው የሚኖሩት፡፡ አንዷ ህንድ፣ ሌላዋ ሎስአንጀለስ፣ አንዷ ደግሞ ኒውዮርክ ነው የምትኖረው፡፡ አያትም ሆኛለሁ፤ በህንድ ሁለት የልጅ ልጆች አሉኝ፡፡ ለ5 ዓመት በህንድ ኖሬያለሁ፣ ይሄ ደግሞ የተለያዩ ባህሎችን ለማወቅ አግዞኛል፡፡ ወደ ትምህርት ሁኔታ ስመጣ በከተማ ፕላን ሁለተኛ ዲግሪ አለኝ፡፡ የመጀመሪያ ዲግሪ በመንግስት አስተዳደር ወስጃለሁ፡፡  በተማርኩባቸው የሙያ መስኮች በተለያዩ የኃላፊነት ደረጃዎችም ሃገሬን አገልግያለሁ፤ በማገልገል ላይም እገኛለሁ፡፡

(Baaxo’gini baaxot yaagiteeh, baaxo abaara) -
የአፋር ተረት

የሚከተለውን የፃፉልን እጓለ ገብረ ዮሐንስ ናቸው፡፡ “የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ” በሚለው መጽሐፋቸው ውስጥ ነው፡፡
በግሪክ ሜቶሎጂ የሚገኝ አንድ ትልቅ ተረት አለ፡፡
(ይህም ስለ ፕሮሚሴቭስ የሚነገረው ነው፡፡ ትልቅ ምሥጢር በውስጡ ደብቆአል፡፡ ፕሮሚሴቭስ በሚል አርእስት የቀድሞውን ተረት መሠረት በማድረግ ኤስሂሎስ የሚባለው ትራጀዲን የፈጠረ ባለቅኔ፣ አንድ ትሪሎጂ - ማለት ሦስት ድራማዎች ጽፎአል፡፡ እሱን በመከተል ሸሊ ባይረን ጌቴ ጽፈዋል፡፡ የፕሮሚሴቭስ መንፈስ በአውሮፓ የመንፈስ ታሪክ ውስጥ መካከለኛውን መሥመር የያዘ ነው፡፡ አሁን የጠቀስናቸው ሰዎች በአውሮፓ የሥነ ጽሑፍ ጠፈር ላይ በጣም ጐልተው የሚታዩ ከዋክብት ናቸው፡፡)
የፕሮሚሴቭስ ተረት እንደሚቀጥለው ነው፡፡ ፕሮሚሴቭስ በከፊል አምላክ፣ በከፊል ሰው የሆነ ሕላዌ ነበር፡፡ በከፊል አምላክ እንደመሆኑ ዐሥራ ሁለቱ የግሪክ አማልክት በኦሉምቦስ ተራራ ሆነው ስለሰውና ስለዓለም አስተዳደር ሲመክሩ ይሰማ ነበር፡፡ በከፊል ሰው እንደመሆኑ የሰው ሥቃይና መከራ በጣም ያሳዝነው፣ ይጸጽተው ነበር፡፡ ሰው ቤት ንብረት ሳይኖረው በበረሃ፣ በጫካ፣ በዱር፣ በገደል፣ በዋሻ፣ በቁር፣ በሀሩር እንዲኖር ተፈርዶበት ነበር፡፡ ይህ መሆኑ አማልክት መክረው ዘክረው ለሰው የዕውቀት ምንጭ የሆነውን ብርሃንን የሰጡት እንደሆን ከዕለታት ባንድ ቀን ሰጭነታቸውን ክዶ በነሱ ላይ በመነሳት የሚያምፅ መሆኑን በመረዳት ብርሃንን ከሰዎች ደብቀው ከማይደርሱበት ቦታ በመሠወራቸው ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ሰዎች በጭለማና የርሱ ተከታይ በሆኑት ችግሮች ሥር ሲሰቃዩ ይኖራሉ፡፡
ይህ የሰዎች መራራ ዕድል ወገናቸው በሚሆን በፕሮሚሴቭስ ላይ ርህራሄ አሳድሮበት ብርሃንን አማልክት አርቀው ከደበቁበት ሰርቆ ለሰዎች ወስዶ ሰጠ፡፡ ያንጊዜ ማናቸውም ነገር ግልጽ ሆኖ ታያቸው፡፡ በብርሃን ምክንያት ጥበብና ማናቸውም የዕውቀት ስልት ስለተገለጸላቸው ራሳቸውን ከገዛ ራሳቸው በተገኘው ዘዴ ለማስተዳደር ጀመሩ፡፡
ፕሮሚሴቭስን ግን ለሰዎች ብርሃንን ሰጥቶ በጐ በመሥራቱ አማልክት ቀንተው በብርቱ ስቃይ ይቀጣ ዘንድ አዳኝ ከማይደርስበት ገደል ላይ ከቋጥኝ ድንጋይ ጋር በሰንሰለት ተቆራኝቶ አሞራ ለዘለዓለም እንዲበተብተው ፈረዱበት፡፡
***
ከፕሮሚሴቭስ ዕጣ -ፈንታ ይሰውረን፡፡ ይህ ፕሮሚሴቭስ የሰውን ዕድል ለማሻሻል የሚታገሉት የዕውቀት ሰዎች፣ የመምህራንና የሊቃውንት ምሳሌ ነው፡፡ እሱ ብርሃንን አማልክት ከደበቁበት ቦታ ወስዶ ለሰው እንዳበረከተ ፣ የዕውቀት ሰዎችም ዕውቀት በመለኮታዊ ምሥጢርነት ከሰው ተደብቃ ስትኖር ሳለ በብዙ ትግል አግኝተው፣ ከገዛ ራሳቸው አሥርፀው የወገኖቻቸውን ዕድል ለማሻሻል ያበረክታሉ፡፡ ዋጋቸውም ሌላ ሳይሆን ስቃይ መከራ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል ሶክራቲስ በመርዝ ተገድሎአል፡፡ ጆርዳኖ ብሩኖ የጧፍ ቀሚስ ተጐናጽፎ በእሳት ተቃጥሎአል፡፡
እነዚህ ሰዎች እንደ ጧፍ መብራት ማለት ናቸው፡፡ ራሳቸው ነደው ተቃጥለው ያልቃሉ፡፡ ለሌሎች ግን ብርሃን ይሰጣሉ፡፡ የፕሮሜሴቭስ ምሳሌ አንድ ትልቅ ሕግ ጉልህ አድርጐ ያሳያል፡፡ ይህም “ዕውቀት በሥቃይ የሚገኝ ነው” (Learn through suffering) የሚል ነው፡፡  
ልጆቻችንን ይህን ለሌሎች ስንል መታገል፣ መሰዋት፣ ማድረግ እንደምን እናስተምር? ብርሃን የሚያመጡ ሰዎች ያስፈልጉናል፡፡ ዕውቀትን ለሀገር ለማጎናፀፍ የሚጥሩ መምህራን ያሹናል፡፡ የዕውቀት ብርሃን ለመጪው ትውልድ ታትሮ ለማለፍ ፣ ልብና ልቡና ይፈልጋል፡፡ አረፍ ብሎ ወዴት እያመራን ነው ብሎ መጠየቅን ግድ ይላል፡፡ ዕውቀት ከትምህርት ብቻ የሚገኝ አይደለም፡፡ ከኑሮአችን፣ ከልምዳችን፣ ከትግላችን እንጂ፡፡ ይህ ወረድ ብሎ አፈሩን መዳሰስን፣ ህዝቡን ማግኘትን፣ የልብ ትርታውን ማወቅን ይጠይቃል፡፡ ምን ጎደለው? ስለዚህ ጉዳይ ግንዛቤ አለ ወይ? በምን ዓይነት መንገድ የጎደለውን ዕውቀት ለማሟላት እችላለሁ? ማለትን ይጠይቃል፡፡ መንገዱን ካገኙ በኋላም፤ ጧት ማታ ሳይታክቱ መታተርን ይጠይቃል፡፡ ይህን ከልብ ካደረግን አገር መውደድ ገብቶናል፡፡ ያንድ ሰሞን ሞቅ ሞቅ ብቻ አገርን ከገባችበት ማጥ አያወጣትም፡፡ “ኦሆ በሀሊ፣ ያርጓጅ አናጓጅ፣ በደመቀበት ቦታ ሁሉ የሚያጨበጭብ አንድም የተለየ ነገር ለማስገኘት አይችልም” ይላሉ ዶክተር እጓለ፡፡ ሉቃስን በመጥቀስም እንዲህ ይሉናል፡- “ውሰብአ አቴናሰ ወእለ ይነግድ ኲሎሙ ህየ በእደ ትካዘ አልቦሙ ዘእንበለ ዳእሙ ለአፅምኦ ወነቢብ ዘሐዲስ”፡፡ አቴናውያን አዲስ ነገር ከመስማት ወይም ከመናገር በስተቀር ሌላ ምኞት አልነበራቸውም፡፡ ባለው ላይ ቆሞ አዲስ ነገር ለማግኘት የሚጣጣር ሰው ሁል ጊዜ ወደፊት ይሄዳል - ማለት ነው፡፡
እንደ አቴናውያን፤ በአለው ላይ ቆመን አዲስ ነገር ለማግኘት የምንጣጣር ከሆነ ወደፊት እንሄዳለን፡፡ ትምህርትንና ዕውቀትን መሰረቱ ያደረገ ትውልድ ከፈጠርን የራሱን ጥያቄ፣ የራሱን ነገ ራሱ ይወልዳል፡፡ የሚኖርበት ቤት ሲጠበው ቤቱን ራሱ አስፋፍቶ ይሰራዋል፡፡ ሁሉን እኛ እናድርግልህ ካልነው - ሁሉን ቀላቢ እንሁንለት ካልን፤ ዞሮ ዞሮ ተቀላቢ ትውልድ ነው የምናፈራው፡፡ ፈረንጆቹ እንደሚሉት - Spoon – Feeding mentality ይጠቀልለዋል - የአጉሩሱኝ አስተሳሰብ እንደማለት ነው፡፡
ለወጣቱ የመንግሥቱ ለማን ግጥም “መርፌ - ትሰራለህን” ማንበብና በዚያ አቅጣጫ መጓዝ የአባት ነው በየትኛውም አቅጣጫ! ወጣቱ በሥነ ምግባር ረገድ፣ የሰውን ፀባይና ችሎታ በሚመረምር መልኩ አዕምሮው መታነፅ አለበት፡፡ ዕውቀትን መሰረት ሳያደርግ ለትግል ብቻ ብናዘጋጀው የፕሮፖጋንዳ ወይም የአጀንዳ ማስተላለፊያ አሸንዳ ቱቦ ነው የሚሆነው፡፡ ይህ በታሪክም የታየ ነው፡፡ በማህበራዊ ኑሮው የእያንዳንዱ መብትና ተግባር የሚጠበቅበት፣ “ሰው በንፁህ ተምኔቱ መሰረት በሰላም ተደስቶ የሚገኝበትን ሕግ” ይዞ መጓዝ እንዳለበት ሊረዳ ይገባል፡፡ ህይወት እንደ ጂኦሜትሪ ትምህርት በቀጥታ መሥመር የተሞላና የተለካ አይደለም፡፡ ቀላል ሂሳብም አይደለም፡፡ እንዴት እንደሚገነባ፣ ከራሱ ህይወት ተነስቶ እንዴት ለማደግ እንደሚችል፣ ትምህርትን ባሰላሰለ መልኩ ማጤን እንጂ “ሳይገሉ ጎፈሬ፣ ሳያረጋግጡ ወሬ” መሆን የለበትም፡፡ እስከዛሬ አጭር ተመልካች፣ አጭር ተጓዥ ሳናደርገው (Myopic) አልቀረንም፡፡ አጭር ግቦች አጭር ያደርጉናል!
አንድ ደራሲ እንደሚለው፤ “… የውጪ ጉዳዮችን ካገር ውስጥ ኃይሎች አሰላለፍ፣ ኢኮኖሚያዊ ችግሮችን ከጥበብ ሽግግርና ከውጪ ርዳታ፣ የቋንቋ መዘበራረቅና ጉራማይሌነትን ከባህላዊ ድቀት፣ የሐሳብ ነፃነትን ከጋዜጣ፣ ራዲዮና አጠቃላይ ውይይት ምህዳር መጥበብ ጋር…” የሚያነፃፅር ወጣትም ሆነ አዋቂ ያስፈልገናል፡፡
ወጣቱ አገሩን ያውቅ ዘንድ ጥልቅ አስተሳሰብ፣ ረዥም ርዕይና በግብረገብ የታነፀ ድፍረትና መስዋዕትነት ያስፈልገዋል፡፡ መጪውን አዲስ ዓመት እንዲህ እናስብ! የሀገራዊነት፣ የወገን አሳቢነት፣ የኢ-ራስ - ወዳድነት፣ የሁሉን - አውድም አስተሳሰብ አለመያዝ፣ ሁሉን - ረጋሚ ያለመሆን አመለካከት፣ ኢፅንፋዊነት ወዘተ እንደመርህም፣ እንደኑሮም ሊሰርፁበት ይገባል፡፡ አለበለዚያ አፋሮች እንደሚሉት “አገሩን የማያውቅ ሰው፣ መሬትን እየረገጠ መሬትን ይረግማል” ይሆናል፡፡                 



  • በ514 የዳስ እና የዛፍ ጥላዎች ትምህርት እየተሰጠ ነው
  • ከ20ሺህ በላይ ስራ አጥና መሬት አልባ ወጣቶች አሉ
  • ከግማሽ በላይ ህዝብ የትራኮማ ተጠቂ ነው

           ከኢህዴን/ብአዴን ዋና ዋና የጦር ማዘዣዎችና መንቀሳቀሻ አካባቢዎች መካከል አንዱ የነበረው የዋግኽምራ ዞን፤ በኢኮኖሚ እድገት ወደኋላ መቅረቱንና ድህነት አለመቃለሉን በመጥቀስ ከአስር አመታት በፊት ለቀድሞው ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ቅሬታ አቅርቦ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን ሰሞኑን በድጋሚ ለፌደራልና ለክልል ባለስልጣናት ምሬቱን ገለጸ፡፡
ባለፈው ቅዳሜ በሰቆጣ ከተማ በተደረገ ውይይት ላይ ቅሬታቸውን ያቀረቡት የአካባቢው ነዋሪዎች፣ ዞኑ በአማራ ክልል ውስጥ ከሚገኙ አስር ዞኖች ጋር ሲነጻጸር፤ በድህነት፣ በጤና ጉድለትና በትምህርት ችግሮች ቀዳሚ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በትምህርት ጥራት ላይ  መጠነ ሰፊ ችግር እንዳለና በዞኑ በ514 ዳሶችና የዛፍ ጥላዎች ውስጥ የአንደኛ ደረጃ ትምህርት እየተሰጠ እንደሚገኝ ነዋሪዎች ገልፀዋል፡፡ ሁለተኛ ደረጃ እና ከዛም በላይ ያሉ ትምህርት ቤቶች በአካባቢው ባለመኖራቸው 32 ሺ ተማሪዎች ትምህርታቸውን ማቋረጣቸውንም አስረድተዋል፡፡
በዞኑ ከተሰሩት ሶስት ሆስፒታሎች አንዱ ብቻ አገልግሎት እንደሚሰጥ፣ ከሃያ ዘጠኝ የጤና ጣቢያዎች አስሩ ከደረጃ በታች በመሆናቸው እንደተዘጉ፤ ከተገነቡት 125  ጤና ኬላዎች  አስሩ ከደረጃ በታች ሆነው ሥራ እንዳቆሙ፣ 6 የግል ጤና ተቋማት ቢኖሩም ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት እንደማይሰጡ ነዋሪዎቹ ገልፀዋል፡፡ ከወሊድ ጋር በተያያዘ በሚከሰት  የእናቶች ሞት ዞኑ ከክልሉ በቀዳሚነት እንደሚጠቀስ፣ ከግማሽ በላይ የሚሆነው ህዝብ  ለትራኮማ በሽታ የተጋለጠና በቤተሰብ አንድ ሰው ለዓይነ ስውርነት የተጋለጠ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡  
የዋግኽምራ ህዝብ ያደረገው የትግል ተጋድሎ ታሪክ የማይረሳ ቢሆንም፣ ከሌሎች ዞኖች ጋር ሲነፃፀር የልማት ተጠቃሚነቱ አነስተኛ ነው  ያሉት አንድ አስተያየት ሰጪ፤ ወደ ትግራይ ክልል ብንካለል ለውጥ እናገኝ ነበር፤ ምክንያቱም አላማጣና ራያና ቆቦ መንገድ ሲሰራ ለእኛም ይሰራልን ነበር ብለዋል፡፡
የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ለቀረቡት ቅሬታዎችና ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ፣ በዞኑ የሚታዩ ችግሮች ተደራራቢ ከመሆናቸው አንፃር ችግሮቹን ከመሰረቱ መቅረፍ አዳጋች መሆኑን ገልፀው፣ ዞኑን የልማት ተጠቃሚ ለማድረግ መሰረት የሚጥሉ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡
ነዋሪዎች ያነሷቸው ችግሮች መኖራቸውን አምነው፣ ይሄም ሆኖ ግን በትምህርት፣ በጤናና በምግብ ልማት ከዚህ ቀደም ከነበረው የተሻለ ለውጥ እየታየ መሆኑንና የልማት ስታራቴጂውን ከግምት ማስገባት እንደሚያስፈልግም አስረድተዋል፡፡ አካባቢው የቱሪስት መስህቦች ያሉት ቢሆንም በድህነት ምክንያት ዝቅ ያለና የተረሳ ዞን መሆኑን ያወሱት የአካባቢው ተወላጅና የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ ካሣ ተ/ብርሃን፤ “ከአካባቢው ተፈጥሮአዊ አቀማመጥ አንጻር ህዝቡ ድህነትን ለማሸነፍ የሚያደርገው ተጋድሎ ተጠቃሽ ነው፣ በትጥቅ ትግሉ ሁላችንም በእግራችን ስንማስን እናውቀዋለን፤ በዞኑ የሚሰሩና የሚኖሩ ህዝቦችን ጥረት አደንቃለሁ” ብለዋል፡፡
የክልሉ ርዕሰ መስተዳደር አቶ ገድሉ አንዳርጋቸው በበኩላቸው፤ ከ5 አመታት በፊት በክልሉ ከሚኖረው 20 ሚ. ህዝብ 2.5 ሚ የሚሆነው የምግብ ዋስትና ያላረጋገጠ እንደነበር ጠቅሰው፤ በአሁኑ ጊዜ 1.4 ሚሊዮን የሚጠጋ ህዝብ በችግሩ ውስጥ እንደሚገኝ ገልፀዋል፡፡ ዋግኽምራ ዞንም በርከት ያለ ህዝብ በየዓመቱ ክረምት በመጣ ቁጥር ተረጂ እንደሚሆንና ዞኑ ስር የሰደደ የምግብ ዋስትና ችግር የሚታይበት በመሆኑ ሁልጊዜም አጀንዳ ሆኖ እንደቀጠለ ተናግረዋል፡፡
በዞኑ የመሰረተ ልማት ችግሮችን ለመቅረፍ 128 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የሰቆጣ ላሊበላ  መንገድ በ2007 ዓ.ም. ለመስራት መታቀዱን ጠቁመው፣ በዞኑ ያሉትን መጠነ ሰፊ ችግሮች ለመፍታት የአካባቢውን ተፈጥሮዊ አቀማመጥ ባገናዘበ መንገድ ህብረተሰቡና መንግስት በቅንጅት እንደሚሰሩ ተናግረዋል፡፡ የስራ አጡን ቁጥር ከመቀነስ አኳያም የተደራጁ ስራ አጦችን በንብ፣ በማር እና በአሳ ምርት በማሰማራት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማስቻል እንቅስቃሴ መጀመሩን አስገንዝበዋል፡፡
የእንስሳትና የአሣ ልማት ምርት፣ የቱሪዝም፣ የብረታ ብረትና ማዕድን መስኮች ላይ ትኩረት አድርጐ መስራት ለዞኑ የተፋጠነ ልማት ለማምጣት ተመራጭ አካሄድ እንደሆነም አቶ ገድሉ  ተናግረዋል፡፡

እንግሊዝን ጨምሮ በተለያዩ የአውሮፓ አገራት ጫት ራሱን የቻለ አደንዛዥ ዕጽ ነው በማለት እንዳይገባ መታገዱን  ተከትሎ ወደ አውሮፓ ይላክ የነበረው ምርት ሙሉ ለሙሉ በመቋረጡ፣ አገሪቱ ለአለማቀፍ ገበያ ከምታቀርበው የጫት ምርት አብዛኛውን የምትሸፍነው አወዳይ ከተማ የኢኮኖሚ ፈተና ውስጥ መውደቋን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘገበ፡፡ለኢትዮጵያ ጫት በሯን በመዝጋት የመጨረሻዋ የአውሮፓ አገር የሆነችው እንግሊዝ፣ ባለፈው ሰኔ ወር ጫትን ህገወጥ ዕጽ በማለት እንዳይገባ መከልከሏን ያስታወሰው ዘገባው፤ ይህም በሺዎች በሚቆጠሩ የአወዳይ ጫት አምራች ገበሬዎች፣ ነጋዴዎችና ላኪዎች ላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ ተጽዕኖ ማድረሱን  ጠቁሟል፡፡
በአወዳይ አካባቢ በጫት ልማትና ንግድ ላይ ተሰማርተው የሚገኙ አርሶ አደሮችንና ነጋዴዎችን ጠቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ እንደዘገበው፤ አብዛኛው የአካባቢው ህዝብ የገቢ ምንጭ ከጫት ጋር የተያያዘ በመሆኑ፣ ክልከላውን ተከትሎ የተከሰተው የገበያ መቀዛቀዝ በአካባቢው እንቅስቃሴ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ፈጥሯል፡፡
እንግሊዝ ጫትን ከመከልከሏ በፊት፣ በወር ከሶስት ቶን በላይ ጫት ወደዚያው ይልክ እንደነበር ያስታወሰው ሙስጠፋ የተባለ በጫት ኤክስፖርት ዘርፍ የተሰማራ ነጋዴ፣ ከክልከላው በኋላ ግን ምርቱን የሚያቀርበው ለአገር ውስጥ ገበያ ብቻ በመሆኑ ገቢው በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱን ለአጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘጋቢ ተናግሯል፡፡ በኬንያም ተመሳሳይ የገበያ ችግር እንደተፈጠረ ተጠቁሟል፡፡
በአወዳይ አካባቢ የሚኖሩ ለውጭ ገበያ የሚላክ ጫት ደላሎች፣ በአንድ ኪሎ ጫት እስከ 30 ዶላር ገቢ ያገኙ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ በአሁኑ ሰዓት ግን ገቢው ወደ 5 ዶላር ማሽቆልቆሉን አመልክቷል፡፡
በጫት ንግድ ዘርፍ የተሰማራ አንድ ሌላ የአካባቢው ነጋዴም፣ አንዳንድ አርሶ አደሮች የገቢውን መላቅ በማየት ሌሎች የእህል አይነቶችን ማምረት ትተው ወደ ጫት እርሻ ጠቅልለው መግባታቸውን በማስታወስ፣ ችግሩ በርካታ የአካባቢውን አርሶ አደሮች እንደሚጎዳ ጠቁሟል፡፡
አገሪቱ በአሁኑ ሰዓት የጫት ምርቷን የምትልከው ሶማሊያና የመንን ለመሳሰሉ አገራት መሆኑን የጠቀሰው አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ፤ እ.ኤ.አ በ2012/13 ጫት በአገሪቱ የኤክስፖርት ምርት ደረጃ የአራተኛነትን ቦታ ይዞ እንደነበርና  270 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደተገኘም አስታውሷል፡፡