Administrator

Administrator

“ከሁሉም በላይ ገጣሚ ነኝ”

ኢ.ካ
አንጋፋው ገጣሚና ደራሲ፣ ተርጓሚና ጸሃፌ ተውኔት ነቢይ መኮንን የናዝሬት ልጅ ነው - ናዝሬት ተወልዶ ያደገ፡፡ ናዝሬትን ከልቡ ይወዳታል- ከእነ አቧራዋ፡፡ በልጅነቱ ፊደል ቆጥሮ ዳዊት ደግሞባታል፤ ዘመናዊ ትምህርት ቀስሞባታል፡፡ የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን የተከታተለው በናዝሬት የአጼ ገላውዲዮስ ት/ቤት ነው፡፡ ስለዚህም ሁሌም ከአፉ አትጠፋም - ናዝሬት፡፡
ገጣሚ፣ ደራሲና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን፣ ከአባቱ ከአቶ መኮንን ወንድምና  ከእናቱ ከወ/ሮ በለጤ በድሉ፣ በነሐሴ ወር 1946 ዓ.ም ነው የተወለደው፡፡ ወደ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከመግባቱ በፊት መምህር ተከስተ ዘንድ  የቄስ ትምህርቱን ተከታትሏል - እስከ ዳዊት ድረስ፡፡   
ነቢይ መኮንን፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እንዳጠናቀቀ በስድስት ኪሎ በሚገኘው ልኡል በእደ ማርያም ተማሪ ቤት ነው የገባው - በጉብዝናው ተመርጦ፡፡ በ1966 ዓ.ም፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሳይንስ ፋኩልቲን የተቀላቀለው ነቢይ፤ ኬሚስትሪ ነበር ያጠናው፡፡ ተማረበት የሙያ  ዘርፍ ግን ሰርቶበት አያውቅም፡፡ መላ ህይወቱን በፍቅር የሰጠውና የተጋው ለኪነጥበብ ሥራዎች ነው፡፡
ነቢይንና ሥራዎቹን በጥልቀት የሚያውቁ ብዙዎች እንደሚመሰክሩት፣ ነቢይ መኮንን  ሁለገብ ከያኒ ነበር፡፡ ያልሰራበትና አሻራውን ያላኖረበት የጥበብ  ዘርፍ የለም፡፡ ከሥነግጥም እስከ ተውኔት፣ ከትርጉም ሥራዎች እስከ የፈጠራ ድርሰቶች ድረስ ተራቆበታል፡፡    
የሥነጽሁፍ ረዳት ፕሮፌሰሩ  የሻው ተሰማ በቅርቡ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ”ሙያና ጥበብ ሲመጋገብ - ከታወቁ ደራስያን ሥራዎች አኳያ“ በሚል ርዕስ ባስነበቡት ጽሁፋቸው፣ ነቢይ ዕውቅና ያተረፈው በብዙ ዘርፍ ነው፤ ይላሉ፡፡
 “--ነቢይ ዕውቅና ያተረፈው በብዙ ዘርፍ ነው፤ ግሩም ችሎታ ያለው ተርጓሚ ነው። --ነቢይ አንቱ የተባለ ገጣሚም ነው። ግጥሞቹ ልብን ይመስጣሉ። በተለይ በግጥሞቹ የሚያነሳቸው ርእሰ ጉዳዮች ከአዲስ እይታ የሚፈልቁና፣ ሀገራዊ አንድምታ ያላቸው ናቸው። በዚያ ላይ የተነገረለት አርታኢም ነው። በ«አዲስ አድማስ» ጋዜጣ ለረጅም ዓመታት በአዘጋጅነት ሲሠራ ያበረከተውን አስተዋጽኦ ያስተዋለ ሰው፣ ጠንካራ አርታኢነቱን ለመመስከር ግንባሩን አያጥፍም።” ሲሉ የነቢይን ሁለገብ ከያኒነት አስረግጠው ይገልጻሉ፡፡     
ነቢይ የትያትርና ድራማ ጸሃፊም ነበር፡፡ ከአስርት ዓመታት በፊት “ባለጉዳይ” የተሰኘ ተወዳጅ የቴሌቪዥን ድራማ ለዕይታ አብቅቷል፤ አንጋፋው አርቲስት አበበ ባልቻ፣ ራሱ ነቢይ መኮንንና ሌሎችም አርቲስቶች የተወኑበት፡፡ ጭብጡ ዛሬም ድረስ ተባብሶ የቀጠለው ከመሬት ጋር የተያያዘ የሙስና ጉዳይ ነው፡፡ ድራማው ከ10 ዓመታት በኋላ በድጋሚ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ቀርቦ፣ እንደ አዲስ በከፍተኛ አድናቆት ነው የታየለት፡፡ ነቢይ ”ናትናኤል ጠቢቡ“ የተሰኘ ተውኔትም ተርጉሞ ለመድረክ አቅርቧል፡፡ “ጁሊየስ ቄሳር” ሌላው ተርጉሞ ለዕይታ ያበቃው የጥበቡ  በረከቱ ነው፡፡
በደርግ ዘመን እንደ እድሜ አቻዎቹ  ሁሉ፣ በጸረ-አብዮተኝነት ተጠርጥሮ ወህኒ የተወረወረው ነቢይ መኮንን፤ ከዛሬ ነገ ይሙት ይትረፍ ሳያውቅ፣ Gone With The Wind የተሰኘውን ዳጎስ ያለ ልብወለድ  መጽሐፍ በሲጋራ ወረቀት ላይ እየተረጎመ፣ በድብቅ በማስወጣት፣ ከእስር  ሲፈታ ነበር፣  “ነገም ሌላ ቀን ነው” በሚል ርዕስ ያሳተመው፡፡
 ይህን አስገራሚ ታሪክ ሰምታ የተደመመች አንዲት አሜሪካዊት ጋዜጠኛ፣ በ1990ዎቹ አጋማሽ ላይ ባህር ተሻግራ አዲስ አበባ በመምጣት፣ ከነቢይ ጋር ሰፊ ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡ እኔ  ደግሞ አሜሪካዊቷ ጋዜጠኛ ወደ ሃገሯ ልትመለስ አንዲት ቀን ሲቀራት አግቼያት ኢንተርቪው በማድረግ፣ ታሪኩን  ለአዲስ አድማስ አንባቢያን አድርሻለሁ፡፡  
“ነገም ሌላ ቀን ነው” የተሰኘው መጽሐፍ የመጀመሪያ ዕትም በሳንሱር ምክንያት መግቢያውና አንዳንድ ሃሳቦቹ ተቆራርጠው መውጣታቸው የሚታወቅ ሲሆን፤ በቅርቡ ሦስት መጻሕፍትን በአንድ ላይ ሲያስመርቅ አብሮ የተመረቀው ህትመት ግን  በፊት ያልታተመው መግቢያ፣ ታክሎበት በአዲስ መልክ ነበር ለንባብ የበቃው፡፡  
በቅርቡ በአንድ ላይ ከተመረቁት ሦስት የነቢይ ሥራዎች አንዱ፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ከዓመት በላይ በተከታታይ ሲቀርብ የነበረውና ከፍተኛ ተነባቢነትን የተቀዳጀው “የኛ ሰው በአሜሪካ” - የተሰኘ የጉዞ ማስታወሻ ነው፡፡ ታሪኩ በአሜሪካ በሚኖሩ ዳያስፖራ ኢትዮጵያውያን አኗኗር ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡ ሦስተኛው መጽሐፍ “የመጨረሻው ንግግር” የተሰኘ ሲሆን፤ The Last Lecture ከሚለው በእውነተኛ ታሪክ ላይ የተመሰረተ መጽሐፍ የተተረጎመ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በአዲስ አድማስ ላይ ተቀራራቢ ጭብጥ ያለው መጽሐፍ ነቢይና እኔ እየተረጎምን በተከታታይ አስነብበናል፡፡ የመጽሐፉ ርዕስ ”ቱስዴይ ዊዝ ሞሪስ” የተሰኘ ሲሆን፤ “ፕሮፌሰሩ” በሚል ርዕስ ነበር ያቀረብነው፡፡     
ሁለገቡ ከያኒ ነቢይ መኮንን፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በሚያወጣቸውና በመድረክ ላይ በሚያቀርባቸው ጥልቅ ሃሳቦችን ያዘሉ ውብ  የሥነግጥም ሥራዎቹ፣ ከፍተኛ አድናቆትንና ዕውቅናን ተቀዳጅቷል፡፡ “ከሁሉም በላይ ገጣሚ ነኝ” የሚለው  ነቢይ፤ “ጥቁር፣ ነጭ፣ ግራጫ ግጥሞች” እና “ስውር ስፌት- (ሁለት ቅጾች)”  የግጥም መድበሎችን ለአንባቢያን አቅርቧል፡፡ በመጻሕፍት አሰባስቦ ከሰነዳቸው የሥነግጥም ሥራዎቹ ሁለት እጥፍ ያህል የሚሆኑት ግን በየቦታው ተበታትነው ነው የሚገኙት፡፡ አሰባስቦ ለህትመት የማብቃት ሥራ ይጠይቃል፡፡    
ነቢይ በደርግ ዘመን በኢህአፓ አባልነቱ ታስሮ ለ10 ዓመታት መከራውን በልቷል፡፡ ነገር ግን ደርግንም ሆነ አገሪቱን ወይም ሌላ ተቀናቃኝን  ሲያማርር፣ ሲወቅስ ወይም ሲረግም ማንም ሰምቶት አያውቅም፡፡ እንደ ብዙዎቹ የጦቢያ ፖለቲከኞች፣ ለኢትዮጵያ ህዝብ ታግዬለታለሁ፣ ደሜን አፍስሼለታለሁ፣ ሞቼለታለሁ ወዘተ እያለ አይመጻድቅም፡፡ በሚመጻደቁትም ይስቃል፡፡ እሱና ዘመነኞቹ በአብዮቱ ወቅት ያሳለፉትን በጎም ሆነ ክፉ፣ ያሁኑ ትውልድ እንዲማርበት፣ ከመጻፍና ከመናገር ቦዝኖ አያውቅም፡፡ ጽንፈኝነትና አክራሪነት እንደማያዋጣ ሲመክር ኖሯል፤ በጽሁፎቹ፡፡ ቁምነገርን በቀልድ እያዋዛ ማቅረብ ይወዳል - በጽሁፉም በንግግሩም፡፡ መድረክ ላይ ከወጣ ታዳሚን በሳቅ ያፈርሳል - አፍ ያስከፍታል፡፡ አንደበቱም ብዕሩም የተባለት የጥበብ ባለሙያ ነበር፡፡
ነቢይ ባህልና ጥበብ አገርን እንደሚለውጥ ጽኑ እምነት ነበራ፡፡ በዚህም እምነቱ ነው አዲስ አድማስ በተለይ ጥበብና ባህል ላይ አተኩራ እንድትሰራ ያደረገው፡፡ የየሳምንቱን ርዕሰ አንቀጽ በተረትና ምሳሌ በመጻፍ ፈር ቀዳጅ ነው፡፡ ባለፉት ዓመታት በመቶዎች የሚቆጠሩ ተረቶችን ጽፏል - ለጋዜጣው ርዕሰ አንቀጽ፡፡ አያሌ የርዕሰ አንቀጽ አንባቢያንንም አፍርቷል፡፡
የሥነጽሁፍ ረዳት ፕሮፌሰሩ የሻው ተሰማ፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ”ሙያና ጥበብ ሲመጋገብ - ከታወቁ ደራስያን ሥራዎች አኳያ“ በሚል ርዕስ ባቀረቡት  ጽሁፋቸው፤ “በርካታ የነቢይ ተደራስያን ነቢይን የሚያውቁት በተለይ በ«አዲስ አድማስ» ጋዜጣ ላይ በሚጽፋቸው ተረቶቹ ነው። ከዶ/ር እንደለ ጌታ ከበደ ጋር ባደረገው አንድ ውይይት ላይ እንዳስተዋልነው፣ በበርካታ መቶዎች የሚቆጠሩ ተረቶችን በጋዜጣው ላይ በርእሰ አንቀጽነት ጽፏል። ይህ ለየት ያለ የርእሰ አንቀጽ ይትበሃል፣ ለጋዜጣው የተለየ የተነባቢነት ሞገስ እንዳጎናጸፈው መናገር ይቻላል።” ብለዋል፡፡
ነቢይ፤ ሃሳብ አዕምሮን ከአዕምሮ የሚያገናኝ ድልድይ ነው ብሎ ያምናል፡፡ ለዚህም ነው የተለያዩ ሃሳቦችና አስተያየቶች በአዲስ አድማስ ላይ ያለገደብ በነጻነት የሚስተናገዱት፡፡ እርሱም  እንደ ጋዜጣው መሥራችና ባለቤት አሰፋ ጎሳዬ ሁሉ ሃሳብን አይፈራም፡፡ ለህዝብና ለአገር የሚጠቅም አንዳች ሃሳብ ያላቸው ወገኖች ሁሉ፣ ሃሳባቸውን እንዲገልጹና እንዲጽፉ ሲያበረታታ ነው የኖረው፤ በዋና አዘጋጅነት ዘመኑ ሁሉ፡፡
አዲስ አድማስን ለምን እንደመሰረቱ ባስረዳበት የመጀመሪያ ርዕሰ አንቀጹ ላይ፤”የጋዜጣ ስራ እንጀምር ያልንበት አንዱ ምክንያት የልባችንን ለመናገር ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት ሌሎቹ ዘንድ የጎደለ የመሰለንን እኛ ልንሞላ ነው፡፡ ‘ምሉዕ በኩላሄ’ (ፍፁም የተሟላ) ያደርገዋል ባንልም፣ የበኩላችንን አስተዋፅኦ ለማድረግ ነው፡፡ ሁላችንም ያለንን ካልወረወርን፤ የአንባቢዎቻችን ገደል - አከል የኢንፎርሜሽን ረሃብ፣ ገርበብ ሊል አይችልምና የፕሬስ እድር ውስጥ ገብተን ጠበል እንጠጣ ብለን ነው” ብሏል፤የዛሬ 24 ዓመት ለንባብ በበቃው  የመጀመሪያው የጋዜጣው ዕትም፡፡  
ከጋዜጣው መሥራቾች አንዱ የነበረው ነቢይ መኮንን፣ ስለ አዲስ አድማስ ዓላማ ሲያስረዳም፤ “የጋዜጣችን አላማ፤ በማህበራዊ፣ በኢኮኖሚያዊና በባህላዊ ጉዳዮች ዙሪያ፤ መሰረታዊ እውቀትን ሊያስጨብጡ፣ አስተዋይና ሀላፊነት ሊሰማቸው የሚችሉ ዜጎችን ለመፍጠር የሚያግዙና ያሉትንም ለማጠናከር የሚበጁ ዜናዎችን በወግ በወጉ ማቅረብ ነው፡፡” ሲል ገልጾታል፤ በርዕሰ አንቀጽ ፅሁፉ፡፡
ለዛሬ በሁለገቡ ከያኒና የአዲስ አድማስ የቀድሞ ዋና አዘጋጅ ነቢይ መኮንን የጥበብ ህይወት ዙሪያ ያጠናቀርኩትን አጭር  የግል ዳሰሳዬን  በዚሁ እቋጫለሁ፤ ዳግም እንደምመለስበት ቃል በመግባት፡፡ ራሱ ነቢይ በአንደበቱ እንደተናገረው፣ ከሁሉም በላይ ግጥም ይበልጥበታል፡፡ ነፍሱ ለግጥም  ታደላለች፤ ገጣሚ የሚለውን መጠሪያም ይወደዋል፡፡ ይህን ከግምት ውስጥ በማስገባት የምንለያየው በራሱ ግጥም ይሆናል፡፡  ከዚያ በፊት ግን ለነቢይ ለቤተሰቦች፣ ወዳጅ ዘመዶችና አድናቂዎች መጽናናትን ከልቤ እመኛለሁ፡፡ የነቢይን ነፍስ ፈጣሪ በአጸደ ገነት ያኑርለት፡፡  
 ለራስ የተጻፈ ወቀሳ
እንጠራራ እንጂ
እንፋለግ እንጂ
ከያለንበቱ
ሰው የለም አንበል፣ አለ በየቤቱ
ምን ቢበዛ ጫናው፣ አንገት ቢያቀረቅር
ምን አፉ ቢታፈን፣ ዝም ቢልም አገር
ምን መሄጃ እስኪያጣ፣ መንገዱ ቢታጠር
ጎበዝ እንደ ጭስ ነው፤ መተንፈሻ አያጣም
ቀን መርጦ ሰው መርጦ መነሳቱ አይቀርም፡፡
(ነቢይ መኮንን፤ አዲስ አድማስ፤  
ግንቦት 9 ቀን 1995 ዓ.ም)

- ነቢይ ተደራራቢ የጤና እክሎች ነበሩበት
- “ነቢይ መኮንን ከሳቅ የተሰራ ሰው ነው
“ከሁሉም በላይ ገጣሚ ነኝ” የሚለው ሁለገብ ከያኒ ነቢይ መኮንን፤ የጥበብ መክሊታቸውን አሟጠው ሳይጠቀሙ ህይወታቸውን በሞት ለሚነጠቁ የጥበብ ሰዎች “የዕድሜ ዕቁብ በኖረ” ሲል በግጥም ምኞቱን አስፍሯል።
….”ምነው ለጥበብ ሰው
 ለበሳል ኪነት ሰው
እቁብ በኖረ፣ ወይ የእድሜ ቀይ መስቀል
የክፉ ቀን ደራሽ፣ አንድ ቀን የሚውል
አንድ የጥበብ መዓልት ለሟች የሚቀጥል
ከባካኝ ጊዜያችን፣ ደቂቃና ሰዓት እየቆነጠርን
ለልባም ፀሃፊ የምንለግስበት፣
ዋ! የዕድሜ ዕቁብ ቢኖር!...”
የአንጋፋው ገጣሚና ደራሲ ነቢይ መኮንን የህልፈት ዜና ድንገተኛ ነበር - አስደንጋጭ። ምንም እንኳን ባደረበት ህመም ህክምና ሲከታተል ቆይቶ፣ ባለፈው ረቡዕ ህይወቱ ማለፉ ከቤተሰቦቹ የተነገረ ቢሆንም፣ ህመሙም ህልፈቱም ዱብ ዕዳ ነበረ - ለብዙዎች። ነቢይ በአንድ ወቅት ታምሞ በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል፣ የጤንነቱን ሁኔታ ይከታተል የነበረ አንድ የህክምና ባለሙያ እንደሚናገረው፤ “ነቢይ ተደራራቢ የጤና እክል ቢገጥመውም ጨዋታ አዋቂነቱን፣ ገጣሚነቱንና አገር ወዳድነቱን አላጎደለበትም።”
ግን አሁን ሳይሆን ያኔ። በቅርቡ በአንድ የቴሌቪዥን ጣቢያ ቀርቦ ራሱ እንደገለፀው፤ ወደ ህንድ አገር ተጉዞ  የልብ ህክምና ያደረገ፤ ሲሆን በህንዳውያኑ የተራቀቁ የህክምና ቴክኖሎጂ መደመሙንም ተናግሯል። እንዲያም ሆኖ የ70 ዓመቱ የዕድሜ ባለፀጋ ነቢይ መኮንን፤ የልብ ህመም፣ ስኳርና፣ ደም ግፊት እንደነበረበት የሆስፒታል ምንጮች ይናገራሉ።
የትኛው ህመሙ ተባብሶ ለህልፈት እንደዳረገው ግን ለማወቅ አልተቻለም፡፡ የቅርብ ወዳጆች እንደሚናገሩት ከሆነ፣ ያልተጨናነቀ ህይወቱ ለሚወደው ገጣሚና ደራሲ ነብይ መኮንን የመጨረሻዎች የህይወት ምዕራፎቹ ተግዳሮት የበዛባቸው ነበሩ። ህመሙን ለመንከባከብና ራሱን ለመጠበቅ ምቹ ሁኔታ አላገኘም የሚሉት ወዳጆቼ፣ የቅርብ ሰው በአጠገቡ እንዳልነበረም ነው የሚናገሩት፡፡
የአዲስ አድማስ ዋና ጋዜጣ አዘጋጅና የሁለገብ ጥበብ ባለቤት የነበረው ነቢይ መኮንን ህልፈትን ተከትሎ ለዓመታት ያበረከታቸውን የኪነጥበብ ስራዎች የሚያደንቁና እውቅና የሚሰጡ በርካታ አስተያየቶች ተንሸራሽረዋል- በማህበራዊ ሚዲያው። በአንጋፋው ገጣሚ ፀሃፊ ተውኔት፣ ተርጓሚና አርታኢ - ነብይ መኮንን ህልፈት እጅጉን ማዘናቸውን የሚገልፁት የጥበብ ወዳጆች፤ ነቢይንና ሥራዎቹን እየዘረዘሩ አድናቆታቸውንና ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ከ1992 ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት አስርት ዓመታት ተወዳጇን አዲስ አድማስ ሳምንታዊ ጋዜጣ ከምስረታ አንስቶ በዋና አዘጋጅነት   የመራው ነቢይ መኮንን፤ ርዕሰ አንቀጽን በተረትና ምሳሌ አዋዝቶ መጻፍን ለመጀመሪያ ጊዜ አስተዋውቋል፤ ለአገራችን ብቻ ሳይሆን ምናልባትም ለተቀረውም ዓለም ጭምር፡፡ ይህም  የጋዜጣው አንዱ መለያ ቀለም በመሆን የዘለቀ ሲሆን፤ በአንባቢያን ዘንድም ተነባቢነትን አትርፎለታል፡፡
ነቢይ መኮንን ከዋና አዘጋጅነቱ ጎን ለጎን ግጥሞችን ይጽፍ ነበር፡፡ ተወዳጅ ታሪክ ያላቸው መጻህፍትን ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ በመተርጎም በተከታታይ ያስነብብ ነበር፡፡ ዘ ዳ ቬንቺ ኮድ ፣ ዉመን አት ፖይንት ዚሮ፣ ቱስዴይ ዊዝ ሞሪሰን (ፕሮፌሰሩ በሚል  ርዕስ) በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡
የገጣሚና ደራሲ ነቢይ መኮንን ቀብር ሥነ-ስርዓት ከትላንት በስቲያ ከሰዓት በአዳማ ተፈጽሟል። ከዚያ በፊት ግን ከረፋዱ አራት ሰዓት ላይ፣ በብሔራዊ ቴአትር ዕውቅ አርቲስቶች፣ ወዳጆቹና ቤተሰቦቹ በተገኙበት የነቢይ አስከሬን የሽኝት መርሃ ግብር ተከናውኗል። በመርሃ ግብር ላይ መድረኩን የመራው የማስታወቂያ ባለሙያው አርቲስት ተስፋዬ ማሞ፤ አንጀት በሚበላ የሐዘን፣ የሙዚቃ ቅንብር ታጅቦ እንዲህ ሲል መድረኩን ከፈተው፣
“የደራሲው ብዕር ታጠፈ!”
ከአርቲስት ተስፋዬ በመቀጠል፣ ዕውቁ ተዋናይና ሁለገብ የመድረክ ሰው አርቲስት ተፈሪ ዓለሙ፤ የነቢይ መኮንንን የሕይወት ታሪክ በንባብ ያቀረበ ሲሆን፤ የተለያዩ ተጋባዥ እንግዶች ስለነቢይ የሚያውቁትንና የተሰማቸውን ምስክርነት ሰጥተዋል።
ሌላው በመድረኩ ላይ ምስክርነታቸውን የሰጡት የነቢይ መኮንን የረዥም ዓመታት ወዳጅ ወግ አዋቂው አቶ በሃይሉ ገብረመድህን  ሲሆኑ፤ ሳግ በተናነቀው አንደበታቸው፣ ምንጊዜም ሲገናኙ እርስ በርስ የሚለዋወጧትን ግጥም በማውሳት፣ “ለእኔ ዛሬ ኮረኮንቻማ ቀን ነው” ብለዋል። “ነቢይ ከሳቅ የተሰራ ሰው ነው” ያሉት አቶ በሃይሉ፣ የነቢይን ጨዋታ አዋቂነት በስፋት አንስተዋል። የነቢይ መኮንን ሁለተኛ ልጅ የሆነችው ራኬብ ነቢይ በተመጠነ ንግግሯ ስለአባቷ ቤተሰባዊ ሰብዕና ተናግራለች። በልጅነታቸው ነቢይ የሚጽፋቸውን ጽሁፎች እንደሚያነብላቸው፣ በነጻነት እንዳሳደጋቸው፣ እንዲሁም ከእነርሱ ጋር የተለየ ቅርርብ  እንደነበረው ገልፃለች። “እኔ እንደእናንተ ብዙም አላገኘሁትም፣ በጣም ነው ያስቀናችሁኝ” ስትልም ልብ የሚነካ መልእክት ልቅሶ እየተናነቃት አስተላልፋለች።
በመጨረሻም የስንብት መርሃ ግብሩ የተደመደመው በጭብጨባ ነበር፤ ነቢይ ላለፉት በርካታ ዓመታት ላበረከተው የጥበብ ሥራዎች ዕውቅና ለመስጠት አስከሬኑ እስኪወርድ ድረስ  ጭብጨባው አዳራሽ ያስተጋባ ነበር።
መርሃ ግብሩ አንጋፋና ወጣት ዕድምተኞች የተገኙበት ቢሆንም፣ በቂ እንዳልሆነ የሙዚቃ ተንታኙ ፍሬስብሃት ሰርጸ ይናገራሉ።
“የዛሬው ስንብት ብዙ ትዝብት ያለው ስንብት ነው። ብዙውን ጊዜ ለክዋኔ ጥበባት ሰዎች ሕልፈት የሚኖረው ዓይነት ታዳሚ አይደለም ዛሬ ያየነው። በጥራት ካየኸው ጥርት ያለ ሊሆን ይችላል። ትልልቅ ሰዎችን አይተናል። ግን ነቢይን የሚያውቀው ሰው ይህ ብቻ ነው ብዬ አላምንም። ከፍ ባለ ሁኔታ ሁላችንም ወጥተን አመስግነን ልንሰናበተው ይገባ ‘ነበር’ የሚል ቁጭት አለኝ ብለዋል። ለነቢይ ክብር ያለው ፕሮግራም በተከታታይ በማዘጋጀት እንደሚያስፈልግም መክሯል።
ለ10 ዓመታት ያህል ከነቢይ ጋር በማዕከላዊ እስር ቤት አብረው የታሰሩት አቶ ግርማ አበራ፣ ከነቢይ ጋር እንዴት እንደተዋወቁ ሲናገሩ፤ “ድርጅት ነው ያስተዋወቀን” ይላሉ። “የቀረውን ዕድሜያችንን እስር ቤት ነው ያሳለፍነው። ነቢይ ከእኔ አንድ ዓመት ቀድሞ ወጣ እንጂ እስከመጨረሻ አብረን ነው የታሰርነው። ከወጣንም በኋላ ቅርርባችን የወንድም ያህል ቀጥሏል - ሲሉ ተናግረዋል።”
ከነቢይ መኮንን ጋር ከ30 በፊት ዓመት እንደተዋወቁ የነገረን  ደግሞ፣ ተዋናይ ኩራባቸው ደነቀ ነው። “ከ30 ዓመት በፊት አዲስ አበባ ውስጥ የተለያዩ ስራዎችን በምንሰራበት ወቅት ‘ጁሊየስ ቄሳር’ን ይዞ ይመጣ ነበር። እኛ ደግሞ፣ ‘የጫጉላ ሽርሽር’ን የምንሰራበት ወቅት ነበር፤ እኔ፣ ጀማነሽ ሰለሞን፣ ተፈሪ ዓለሙ፣ ሙሉዓለም ታደሰ፣ መንበረ ታደሰ...ወዘተ በዚያ ጊዜ እርሱ እዚያ አዘውትሮ ይመጣ ስለነበር የዚያን ጊዜ ነው የተዋወቅነው” ሲል አውግቶናል።
ገጣሚ ኤፍሬም ስዩም ደግሞ እንዲህ ይላል። “እኔ ነቢይን የማውቀው... በሚሰራቸው ስራዎች ነበር። ከዚያ በኋላ ነው እርሱን ለማወቅ ፍላጎት ያደረብኝ። አዲስ አድማስ ጋዜጣ ቅዳሜ ቅዳሜ ሳነብ፣ ከአምዶቹ ውስጥ ‘የግጥም ጥግ’ የሚል አምድ ነበር። ይህ አምድ  አሁን ያለነውን ገጣሚያን መንፈስ ከፍ ያደረገና ያነሳሳ ክፍል ነው። የመጀመሪያ ትውውቄ እርሱ ነው። ከዚያ በኋላ በተለያዩ መድረኮችና አጋጣሚዎች የምንገናኝባቸው ነገሮች ይፈጠሩ ነበር።  ወዳጅነታችን እንደዚህ ነው የተጀመረው።” ሲል  ተናግሯል።
የተወዳጁ የኪነት ሰው ነቢይ መኮንን  አስከሬን በብሔራዊ ቴአትር ሽኝት ከተደረገለት በኋላ በቀጥታ ያመራው ወደሚወዳት የትውልድ ቀዬው ናዝሬት/አዳማ ነው - በኑዛዜው መሰረትም የሚወዳቸው ወላጅ እናቱ ባረፉበት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስከሬኑ አርፏል። ከቀኑ 9 ሰዓት ላይ በተፈፀመው የቀብር ሥነ-ስርዓት ላይ ቤተሰቦቹ፣ ወዳጆቹና የሚወዳቸው አድናቂዎቹ በ70 ዓመቱ ህይወቱ ያለፈው ነቢይ መኮንን ባለትዳርና የሦስት ሴት ልጆች አባት ነበር።
በማህበራዊ ሚዲያ “የአዲስ አድማስ እንቁ ነቢይ መኮንን አለፈ” ሲል አስተያየቱን ያሰፈረው ኤልያስ የተባለ አድናቂ፣ “አገሬ ኢትዮጵያ ዛሬ ቀን ጎድሎባታል…. ወጓን ጠብቆና ሰብኮ የኖረ ዐቃቤ ጥበቧን በሞት ተነጥቃች” ሲል ሃዘኑን ገልጿል።

በኢትዮጵያ በተለያዩ የአገሪቱ ከተሞችና ገጠራማ አካባቢዎች ተጠልለው የሚገኙ 4 ነጥብ 5 ሚሊየን የአገር ውስጥ ተፈናቃዮች መኖራቸው ተገልጿል።
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት (ተመድ) የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ቢሮ (ኦቻ) ባወጣው ሪፖርት መሰረት፣ አብዛኛዎቹ ተፈናቃዮች የሚገኙት በሶስት ክልሎች ውስጥ “ነው” ተብሏል። እነዚህም ክልሎች ሶማሊያ፣ ኦሮምያና ትግራይ እንደሆነ ተነግሯል።
አብዛኛዎቹ ቀያቸውን ጥለው እንዲፈናቀሉ ያደረጋቸው ምክንያት፣ በአገሪቱ የተከሰቱ ግጭቶች መሆናቸውንም ቢሮው አመላክቷል።
ቀያቸውን ጥለው ከተፈናቀሉ የአገሪቱ ዜጎች ውስጥ 56 በመቶ የሚሆኑት ቤታቸውን ጥለው ከወጡ፣ ሶስት ዓመት “ሞልቷቸዋል” ሲል ቢሮው አመልክቷል።
ከእነዚህም ውስጥ 23 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ ከሁለት እስከ አራት ዓመት እንደሆናቸው ተጠቅሷል። 11 በመቶ የሚሆኑት ደግሞ፣ ከቀያቸው ከተፈናቀሉ አምስት እና ከዚያ በላይ ዓመታት ማስቆጠራቸውን ጠቁሟል።
ከጥር 2014 ዓ.ም. ወዲህ 3 ነጥብ 3 ሚሊየን የሚሆኑ ተፈናቃዮች ወደ መኖሪያቸው እንዲመለሱ መደረጉን ያስታወቀው ማስተባበሪያ ቢሮው፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች ቀያቸውን ጥለው የሚፈናቀሉ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ፣ በአገሪቱ የተፈናቃዮች ቁጥር 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን መድረሱን አስታውቋል።
በርካታ ተፈናቃዮች በተለይም ደግሞ ለተራዘመ ጊዜ ከቀያቸው ተፈናቅለው የቆዩ ዜጎችን የተወሰነ ድጋፍ ተደርጎላቸው እንዲመለሱ ወይም ደግሞ አሁን ተጠልለውባቸው በሚገኙባቸው አካባቢዎች ካሉ የማሕበረሰብ ክፍሎች ጋር ኑሮ መስርተው እንዲኖሩ ማድረግ አለያም ደግሞ ወደ ሌላ አከባቢ እንዲዛወሩ ማድረግ እንደሚቻል ያካሄደውን ጥናት ዋቢ በማድረግ ቢሮው አመላክቷል።

ከግጭት ለመውጣት ሰላማዊ ውይይት
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ ከሃላፊነታቸው መነሳታቸው ተገልጿል። ኮሚሽነሩ ከሃላፊነታቸው የተነሱት በትናንትናው ዕለት ሰኔ 28 ቀን 2016 ዓ.ም. ነበር።
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈጉባዔ ታገሰ ጫፎ ፅሕፈት ቤት ተገኝተው ይፋዊ ስንብት የተደረገላቸው ዶ/ር ዳንኤል፣ የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ሆነው የተሾሙት ሰኔ 25 ቀን 2011 ዓ.ም. መሆኑን ለማወቅ ተችሏል።
ኮሚሽኑ በተለያዩ ጊዜያት የመንግስት ሃይሎች “ፈጽመዋቸዋል” ያሏቸውን የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች በመመርመር ያመለክታሉ። የተለያዩ ዘገባዎችንና መግለጫዎችን ባልተለመደ ድፍረት በማውጣት ቆይቷል። ከመንግስት ጫና እንደሚያደርስበት የሚገልጹ ዘገባዎች፤ ተደጋጋሚ ስሞታዎችን ቢያቀርብም፣ ይፋዊ ምላሽ እንዳልተሰጠው ያመለክታሉ።
በአማራ ክልል በፋኖ ታጣቂዎችና የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች መካከል የተቀሰቀሰውን ግጭት ተከትሎ፣ የተፈጸሙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን የዘገበ ሲሆን፣ መራዊ እና ጅጋ ከተሞችን ጨምሮ በተለያዩ ከተሞች “ተፈጸሙ” ስለተባሉ የጅምላ ግድያዎች የምርመራ ሪፖርቶችን ይፋ ማድረጉ አይዘነጋም።
የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦ.ነ.ግ.) የፖለቲካ ኦፊሰር አቶ በቴ ኡርጌሳ ለግል ጉዳያቸው በሄዱባት፣ መቂ ከተማ መገደላቸው እንደተሰማ ምርመራ ያደረገው ኮሚሽኑ፣ የምርመራ ግኝቱን ለሕዝብ እንዳይቀርብ ከኦሮሚያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ጫና እንደተደረገበት አዲስ ስታንዳርድ ምንጮቹን ጠቅሶ ዘግቦ ነበር።
ላለፉት አምስት ዓመታት ኢሰመኮን የመሩት ዶ/ር ዳንኤል፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ወደ ስልጣን ከመምጣታቸው አስቀድሞ የሂዩማን ራይትስ ዎች ምስራቅ አፍሪካ ተወካይ የነበሩ ሲሆን 1997 ዓ.ም. የፖለቲካ ቀውስ ተከትሎ ከሌሎች መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ሰራተኞች ጋር ለእስር ተዳርገውም ነበር።
ኮሚሽነሩ ከሃላፊነታቸው የተነሱት የስራ ዘመናቸው ስላበቃ እንደሆነ ተገልጿል።
በተያያዘ ዜና፣ ዶ/ር ዳንኤል በቀለ “በአገር አቀፍ ደረጃ ከግጭት ለመውጣትና መጠነ ሰፊ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶችን በዘላቂነት ለመፍታት ሰላማዊ ውይይትና ምክክር ማድረግ ያስፈልጋል” ብለዋል። ተሰናባቹ ኮሚሽነር መልዕክታቸውን ያስተላለፉት፣ ትናንት በይፋ በቀረበው በ3ተኛው የኢትዮጵያ ዓመታዊ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ሪፖርት ላይ ነው።


ገጣሚ፣ ደራሲና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን፣ ከአባቱ ከአቶ መኮንን ወንድም እና  ከእናቱ ከወይዘሮ በለጤ በድሉ፣ በነሐሴ ወር 1946 ዓ.ም፣ በቀድሞዋ ናዝሬት፣  በአሁኑ አዳማ ከተማ ተወለደ፡፡
 ወደ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ከመግባቱ አስቀድሞ፣ መምህር ተከስተ ጋር የቄስ ትምህርቱን የተከታተለ ሲሆን፤ እዚያም ሳለ ዳዊትን በቃሉ በመሸምደድ የማስታወስ ችሎታውን አዳበረ፡፡  
 የአንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን እዚያው ናዝሬት በአጼ ገላውዲዮስ ት/ቤት  የተከታተለው ነቢይ መኮንን፤ በትምህርት አቀባበሉም ከጎበዞቹ ተርታ የሚሰለፍ ነበር፡፡ ለዚህ ደግሞ ለትምህርት ጥልቅ ፍቅር የነበራቸው  የገንዘብ ሚኒስቴር ባልደረባ የነበሩት አባቱ፤ ጉልህ ሚና ነበራቸው፡፡  ልጃቸው ሁልጊዜም  በትምህርቱ ብርቱ ሆኖ  ምክራቸውን  ይለግሱት  ነበር፡፡ ነቢይም፣ ከክፍሉ አንደኛ በመውጣት አባቱን ከማስደሰት ቸል ብሎ አያውቅም፡፡  ነቢይ አባቱን አቶ መኮንን ወንድምን በሞት ያጣው  የ7ኛ ክፍል ተማሪ ሳለ ነበር፡፡
ነቢይ መኮንን፣ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን  እንዳጠናቀቀ፣ ስድስት ኪሎ በሚገኘው ልኡል በእደ ማርያም ተማሪ ቤት ከገቡ ጎበዝ ተማሪዎች አንዱ ነበር፡፡  በመቀጠልም በ1966 ዓ.ም፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሳይንስ ፋኩልቲን የተቀላቀለው ነቢይ፤ ኬሚስትሪን በዋናነት (ሜጀር)፣ ሂሳብን ደግሞ  ማይነር በማድረግ አጥንቷል፡፡  
እንደ ዘመነኞቹ  በወቅቱ  የተማሪዎች  ንቅናቄ ውስጥ ተሳትፎ የነበረው ነቢይ መኮንን፤ ከደርግ ወጥመድ አላመለጠም፡፡ በኢህአፓ አባልነቱ ታስሮ ለ10 ዓመታት መከራውን በልቷል፡፡ ነገር ግን ደርግንም ሆነ አገሪቱን ወይም ሌላ ወገን ሲያማርር፣ ሲወቅስ ወይም ሲረግም ተሰምቶ አይታወቅም፡፡  እንደ ብዙዎቹ ፖለቲከኞች፣ ለኢትዮጵያ ህዝብ ታግዬለታለሁ፣ ሞቼለታለሁ ወዘተ እያለም መመጻደቅ አያውቅበትም፡፡  በሚመጻደቁትም ይስቃል፡፡ እሱና ዘመነኞቹ በአብዮቱ ወቅት ያሳለፉትን በጎም ሆነ ክፉ፣ ያሁኑ ትውልድ እንዲማርበት ከመጻፍና ከመናገር ግን  ቦዝኖ አያውቅም፡፡ ጽንፈኝነትና አክራሪነት እንደማያዋጣ ሲመክር ኖሯል፤ በጽሁፎቹ፡፡    
 ነቢይ፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ኬሚስትሪ ያጠና  ቢሆንም፣ በገጣሚነት፣ በደራሲነት፣ በተርጓሚነትና በጋዜጠኝነት  በርካታ ሥራዎችን ለአንባቢያን  ያበረከተ ታላቅ የኪነ ጥበብ ባለሙያ ነበር።
በ1992 ዓ.ም ህትመት የጀመረችውን አዲስ አድማስ ጋዜጣን ከመሰረቱት አንዱ የነበረው አንጋፋው የጥበብ ባለሙያ  ነቢይ መኮንን፤ ለሁለት አስርት ዓመታት ጋዜጣዋን በዋና አዘጋጅነት በመምራት፣ ከሥራ ባልደረቦቹ ጋር ስኬታማ አድርጓታል፡፡ የአዲስ አድማስ ዋና አዘጋጅ የነበረው ነቢይ፣ በጋዜጣው ላይ በየሳምንቱ በተረትና ምሳሌ እያዋዛ በሚጽፋቸው ርዕሰ አንቀጾች ታዋቂነትን ያተረፈ ሲሆን፤ ለጋዜጣዋም ተነባቢነትን አቀዳጅቷታል፡፡  
ሁለገቡ ከያኒ ነቢይ መኮንን፣ ከአሰርት ዓመታት በፊት “ባለጉዳይ” የተሰኘ ተወዳጅ የቴሌቪዥን ድራማ ለዕይታ ከማብቃቱም በላይ በትወናም ተሳትፎበታል፡፡ የእዚህ ተከታታይ ድራማ ጭብጥ ከመሬት ጋር የተያያዘ የሙስና ጉዳይ ሲሆን፣ ታዋቂዎቹ ተዋናዮች  አበበ ባልቻ፣ ፈቃዱ ተክለማሪያምና ፍቅርተ ጌታሁንን ጨምሮ ሌሎችም ተሳትፈውበት ነበር፡፡
ነቢይ፣ “ናትናኤል ጠቢቡ” እና “ጁሊየስ ቄሳር” የተሰኙ ተውኔቶችንም ተርጉሞ ለመድረክ አቅርቧል። ”ባለካባ እና ባለዳባ” በተሰኘ ተውኔት ላይ ደግሞ በትወና ተሳትፏል።
“ከሁሉም በላይ ገጣሚ ነኝ” የሚለው ነቢይ መኮንን፤ “ጥቁር፣ ነጭ፣ ግራጫ ግጥሞች” እና “ስውር ስፌት- (ሁለት ቅጾች)” የግጥም መድበሎችን ለንባብ  አብቅቷል፡፡  
ነቢይ፤ “የኛ ሰው በአሜሪካ” - የተሰኘ የጉዞ ማስታወሻው፣ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ ሲወጣ ቆይቶ፣ በመጨረሻ  በመጽሐፍ ተዘጋጅቶ ለህትመት የበቃ ሌላኛው ሥራው ነው። ለንባብ የበቃው ሌላው  የነቢይ መጽሐፍ ደግሞ “የመጨረሻው ንግግር” የተሰኘ ሲሆን፤ “ዘ ላስት ሌክቸር” ከሚለው መጽሐፍ የተተረጎመ  ነው።
ነቢይ፤ ዳን ብራውን የጻፈውንና በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ መነጋገሪያ ሆኖ የነበረውን "The Davinci Code" የተሰኘ መጽሐፍ ወደ አማርኛ ተርጉሞ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በተከታታይ አስነብቧል፡፡  
ከነቢይ ጥበባዊ ሥራዎች  ሌላው  የሚጠቀሰው  "ማለባበስ ይቅር" ነው፡፡ ኤች አይቪ-ኤይድስ  የሀገር አደጋ በሆነበት ዘመን፣ ነቢይ መኮንን "ከቫይረሱ ጋር የሚኖሩትን ማግለል በሽታውን ያባብሳል፤ ስለዚህ ፍቅር እንስጣቸው፤ አናግልላቸው"  የሚል መልእክት ያዘለ  ግጥም ገጥሞ  ታዋቂ ወጣት ዘፋኞች አቀንቅነውታል፡፡  "ማለባበስ ይቅር" የተሰኘው የሙዚቃ ሥራ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በተደጋጋሚ ይታይ እንደነበር ይታወቃል፡፡
ከ32 ዓመት በፊት ሜጋ ኪነጥበባት ማእከልን ከመሰረቱት አንዱ የነበረው ነቢይ መኮንን፤ በጊዜው በሜጋ ኪነጥበባት ማእከል አሳታሚነት ትወጣ የነበረችውን  ‹‹ፈርጥ›› የኪነ-ጥበብ መጽሄትንም በዋና አዘጋጅነት በመምራት ይታወቃል፡፡
ነቢይ፣ ከጋዜጠኝነቱና ከጥበብ ሥራው ጋር በተገናኘ የተለያዩ የዓለም አገራትን የመጎብኘት ዕድል የገጠመው ሲሆን፤ ከጎበኛቸው ሀገራት  መካከልም ፈረንሳይ፣ ጀርመን፣ አሜሪካ፣ ኢራን፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ዛምቢያ፣  ኬንያና   ሱዳን ይገኙበታል፡፡
ነቢይ ለሀገሩ ኪነጥበብ ማደግ ከወጣትነቱ ጀምሮ ብዘ የለፋ ታላቅ የሀገር ባለውለታ እንደመሆኑ መጠን፣ ይህንኑ ግምት ውስጥ በማስገባት፣ የቅርብ ወዳጆቹ ግንቦት 30 ቀን 2011 ዓ.ም፣ በአዲስ አበባ ቴአትርና ባህል አዳራሽ፣ ነቢይ በሀገሩ ይከበራል የሚል  የምስጋና መሰናዶ አዘጋጅተውለት ነበር፡፡  
.ከሁሉ ወዳጅና  ተግባቢ የነበረው ነቢይ መኮንን፣ ባለትዳርና  የሦስት ሴት  ልጆች አባት ነበር፡፡ አንጋፋው ገጣሚ፣ ደራሲና ተርጓሚ ነቢይ መኮንን፣ ባደረበት ህመም በህክምና ሲረዳ ቆይቶ፣ ረቡዕ ሰኔ 26 ቀን  2016 ዓ.ም  በተወለደ በ69 አመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡ ለቤተሰቦቹ፣ ለወዳጅ ዘመዶቹና ለአድናቂዎቹ  መጽናናትን እንመኛለን፡፡

 አንዳንድ ጊዜና ሁኔታዎች አሉ፤ መሀሉን ትታችሁ ውጤቱን ብቻ የምትናገሩበት። ብቻ ግን ከቻላችሁ ደግ ተግባር ስሩ ፤ ከቻላችሁ። እኔ ሁሌም መልካምነት የልብ መሻቴ ነው። በተግባር ግን እንደ ልቤ አይደለሁም። ክፉም ባልሆን ደግ ግን አይደለሁም።

መልካምነት የእውቀት ሳይሆን የመሰጠት ጉዳይ ነው። አሁን ይኸው ሁለቱም (አሰፋም ፣ ነቢይም) በሕይወት የሉም። አሰፋ ጎሳዬ ( የ"አዲስ አድማስ" ጋዜጣ ባለቤት ) የተባለ እጅግ የበዛ መልካም ሰው፣ በነቢይ ሕይወት ላይ ያለውን ድርሻ የምናውቅ እናውቀዋለን። ነፍስን መቁረጥ የፈጣሪ ድርሻም ቢሆን፣ በሰውኛ ስሌት የነቢይ ሕይወት እዚህ እንዲደርስ የአሰፋ ጎሳዬ ድርሻ የበዛ ነው። (" አሴዋ " ይለዋል ግሩም ዘነበ።)

አሴዋ ከተለየን ብዙ ዓመታት ተቆጥረዋል። በነቢይ ሕይወት ላይ ያለው የመልካምነት ድርሻ ግን እስከ ትናንትናዋ ዕለት የደረሰ ነው። አሴዋ፤ ስለ መልካምነትህ የምናውቅ እናስታውስሀለን።

          የሁለታችሁንም ነፍስ ይማር!

(ቴዎድሮስ ተ/አረጋይ)

ሰው ካልሞተ አይመሰገንም የሚሉት ብሂል ትክክል መሆኑን ዛሬ በተጨባጭ አረጋገጥኩኝ፡፡ ለምን እስከዛሬ ስለ ቅርብ ወዳጄ ነቢይ መኮንን የማውቀውን በጎነትና መልካምነት አልመሰከርኩም ብዬ ራሴን ስጠይቅ፣ በተደጋጋሚ ያገኘሁት  ምላሽ፣ ”ንፉግነት” የሚል ሆኖ አገኘሁት፡፡ በዚህም ራሴን ክፉኛ ወቀስኩት፡፡ በጸጸት ተቃጠልኩ፡፡ በራሴም አፍሬ የምገባበት ጠፋኝ፡፡  

የሰው ልጅ ኖሮ ኖሮ ማለፉ እንደማይቀር እያወቅን፣ ለምን ይሆን በህይወት ሳለ በጎነቱን  ተንፍሰን፣ በአደባባይ የማናመሰግነው? (ጥያቄውም ወቀሳውም ለራሴ ነው!) ያንን ያደረገ መቼም የታደለ ነው - የተባረከ!! ቢያንስ እንደኔ በጸጸት ከመሰቃየት ይድናል፡፡ በቁጭት ከመብሰልሰል ይተርፋል፡፡ እንደኔ በራሱ ከማፈር ራሱን ይታደጋል፡፡ የህሊና ሰላም ይቀዳጃል፡፡ በወዳጁ ህልፈት የተሰማውን ሃዘን ብቻ ያስተናግዳል - አልቅሶም ሃዘኑን በእንባው ይወጣል፡፡ የእኔ ዓይነቱ ግን ሃዘኑና ህመሙ  ሁለት ነው፡፡

ስለ ነቢይ መኮንን በህይወት እያለ ለመናገር ያልደፈርኩትን፣ በዚህ መሪር የሃዘን ስሜት ውስጥ ሆኜ በጥቂቱም ቢሆን ልተንፍሰው - ምናልባት ከጸጸት ፈውስ ቢሆነኝ፡፡ ከ20 ዓመታት በላይ በቅርበት  የማውቀው የልብ ወዳጄ ነቢይ መኮንን፣ በደግነት የተትረፈረፈ ሰው ነበር፡፡ እኔ ዛሬ ላለሁበት ደረጃ የደረስኩት፣ በአሰፋ ጎሳዬና በነቢይ መኮንን የተትረፈረፈ ደግነት ነው፤ በሁለቱ የአዲስ አድማስ ዕንቁዎች፡፡ እግሬ የአዲስ አድማስ  ግቢን ከረገጠበት ዕለት ጀምሮ፣ ሁለቱም በጓደኝነት ነበር የተቀበሉኝ - በፍቅር፡፡

አዲስ አድማስን ከተቀላቀልኩበት ጊዜ ጀምሮ ከ15 ዓመታት በላይ ከነቢይ አጠገብ ተለይቼ አላውቅም፡፡ መጀመሪያ ላይ የተቀጠርኩት በከፍተኛ ሪፖርተርነት ቢሆንም፣ ከጋዜጣው ዋና አዘጋጅ ከነቢይ መኮንን ቢሮ ውጭ የሰራሁበትን ጊዜ አላስታውስም፡፡ አንድ ቢሮ ውስጥ መሥራት ብቻ ግን አይደለም፤ ሦስታችንም ምሣ የምንበላው አንድ ላይ ነበር - የጋዜጣው መሥራችና ባለቤት አሴ፣ ዋና አዘጋጁ ነቢይ መኮንንና ከፍተኛ ሪፖርተሩ እኔ፡፡ ሁለቱም ደግሞ አንድም ቀን አለቆቼ መስለው ተሰምቶኝ አያውቅም፡፡ እንደ ቅርብ ወዳጅ እንጂ እንደ አለቃ ቆጥሬአቸው አላውቅም - ዛሬም ድረስ የሚሰማኝ እንዲሁ ነው፡፡

የእኔና የነቢይ መኮንን ቅርርብ ከቢሮም ይሻገራል - የቤተሰቡም አባል ነበርኩ፡፡ በሳምንት ሁለት ወይም ሦስት ቀን አዳሬ ነቢይ ቤት ነበር - በተለይ የጋዜጣው ሥራ በሚበዛበት ዘወትር ሃሙስ፡፡ ባለቤቱና ልጆቹ ለእኔ ፍቅር ነበሩ፡፡ ለአንድ ሳምንት እንኳን ከጠፋሁ ባለቤቱ ደውላ ትቆጣኝ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ ነቢይና ባለቤቱ ዘመድ ጥየቃ ክፍለ ሃገር ቢሄዱ እኔን አስከትለው ነበር፡፡

ነቢይ መኮንን የሙያ አባቴም ነበር - ኮትኩቶ ለዛሬ የሙያ ማንነቴ ያበቃኝ፡፡ ከእርሱ ሥር ተቀምጬ ስለ ጋዜጣ አሰራር፣ ስለ አርትኦት፣ ስለ አጻጻፍ፣ ስለ ግጥም፣ ስለ ትርጉም ሥራ ወዘተ--- ተምሬአለሁ፡፡ እንዲያም ሆኖ አንድም ቀን ነቢይ አለቃዬ መስሎ ተሰምቶኝ አያውቅም፡፡ በዕድሜና በዕውቀት የትናየት ብንራራቅም፣ ነቢይ ሁሌም ለእኔ  ጓደኛዬ ነበር - የልብ ወዳጄ፡፡

በጠለቁና በረቀቁ  ግጥሞቹ ስሙ የናኘው  ነቢይ መኮንን፤ ከልቡ ሰው ነበር - የሰው መጨረሻ፡፡

በተባ ብዕሩና በውብ ቋንቋው የሚታወቀው ነቢይ መኮንን፤ የደግነት ጥግ ነበር - ደግነት የተትረፈረፈው፡፡

በደርግ ዘመን ለአስር ዓመት በእስር ማቆ ከሞት የተረፈው ነቢይ መኮንን፤ የማይሞቀው የማይበርደው ሰው ነበር - ሃዘኑም ደስታውም የተመጠነ፡፡

ዛሬ እንግዲህ ይህን የአዲስ አድማስ ሌላውን እንቁ አጥተነዋል፡፡

 ፈጣሪ ነፍሱን በአጸደ ገነት ያኑርለት፡፡

ለቤተሰቦቹ፣ ለወዳጅ ዘመዱና ለአድናቂዎቹ መጽናናትን ከልቤ እመኛለሁ፡፡

(-ኢዮብ ካሣ-)

ከአዲስ አድማስ  መሥራቾች አንዱ የሆነውና በዋና አዘጋጅነት ጋዜጣዋን በመምራት ተወዳጅ ካደረጓት በቀዳሚነት የሚጠቀሰው ገጣሚ፣ ተርጓሚና ደራሲ ነቢይ መኮንን፣ ከዚህ ዓለም በሞት መለየቱን ስንገልጽ፣ በጥልቅ ሃዘን ውስጥ ሆነን ነው፡፡

 ገጣሚና ደራሲ ነቢይ መኮንን ባደረበት ህመም ህክምና ሲከታተል ቆይቶ፣ ድንገት ያረፈው ዛሬ ሰኔ 26 ቀን 2016 ዓ.ም  ረፋዱ ላይ ነው፡፡

የአዲስ አድማስ ዝግጅት ክፍል፣ የጋዜጣው መሥራችና ዋና አዘጋጅ በነበረው ነቢይ መኮንን ድንገተኛ ህልፈት የተሰማውን ጥልቅ ሃዘን እየገለጸ፤ ለቤተሰቦቹ፣ ወዳጆቹና አድናቂዎቹ መጽናናትን ከልብ ይመኛል፡፡

•  ተቃዋሚዎች “ፕሬዚዳንቱ ከሥልጣን ይልቀቁ“ እያሉ ነው

የኬንያው ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ፣ የኑሮ ውድነትን እንዲያሻቅብ ያደርገዋል የተባለውንና ላለፉት ሁለት ሳምንታት ለተቀሰቀሰው ህዝባዊ  ተቃውሞ ሰበብ የሆነውን የፋይናንስ ረቂቅ በፊርማዬ አላጸድቅም ብለው  ወደ ፓርላማ ቢመልሱትም፣ ተቃውሞው አሁንም  አልበረደም፡፡ በዛሬው ዕለት በናይሮቢና በሌሎች ከተሞች ለተቃውሞ የወጡ ኬንያውያን ፕሬዚዳንቱ ከሥልጣን እንዲለቁ ጠይቀዋል፡፡

ባለፉት ሁለት ሳምንታት በመላ አገሪቱ በተቀጣጠለው ተቃውሞ ሳቢያ፣ ቢያንስ 39 ሰዎች መሞታቸውን የአገሪቱ የሰብአዊ መብት ተቋም አስታውቋል፡፡

በዛሬው ዕለት ማክሰኞ በናይሮቢና በሌሎች የአገሪቱ ከተሞች ተቃውሞው የቀጠለ ሲሆን፤ ፖሊስ ተቃዋሚዎች ላይ አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ ተቃውሞውን ለመበተን ሞክሯል - የተሳካለት ግን አይመስልም፡፡ ተቃዋሚዎችና ፖሊሶች ተፋጠው ነው የዋሉት ተብሏል፡፡

ፕሬዚዳንት ዊሊያም ሩቶ ሃሳባቸውን በመለወጥ በፋይናንስ ረቂቅ ህጉ ላይ ፊርማቸውን በማኖር ሊያጸድቁት ይችላሉ የሚል ስጋት በተቃዋሚዎች ዘንድ  ያረበበ ሲሆን፤ አንዳንድ ተቃዋሚዎች ሩቶን በብልሹ አስተዳደር እየከሰሱና ከሥልጣን እንዲለቁ እየጠየቁ ይገኛሉ፡፡


ፕሬዚዳንቱ ከኬንያውያን ጋር ለመወያየት ጥያቄ ቢያቀርቡም፣ የተቃውሞው ንቅናቄ አባላቱ ግን የሩቶን የእንወያይ ጥያቄ ውድቅ አድርገውታል፡፡

“ሰዎች በጎዳናዎች ላይ እየሞቱ ነው፤ እሱ (ሩቶ) የሚያወራው ግን ስለ ገንዘብ ብቻ ነው፡፡ እኛ ገንዘብ አይደለንም፡፡ እኛ ሰዎች ነን፡፡ እኛ የሰው ልጆች ነን፡፡” ሲል ለሮይተርስ የተናገረ አንድ የሞምባሳ ተቃዋሚ፤ “ፕሬዚዳንቱ ለህዝቦቹ ማሰብ አለበት፤ ምክንያቱም ለህዝቦቹ የማያስብ ከሆነ እኛም ወንበሩ ላይ እንዲቀመጥ አንፈልግም፡፡” ብሏል፡፡

የኬንያ ብሔራዊ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ባወጣው መግለጫ መሰረት፣ ባለፉት ሁለት ሳምንታት በመላ አገሪቱ በተቀጣጠለው ተቃውሞ ሳቢያ፣ ቢያንስ 39 ሰዎች በፖሊስ በተተኮሰ ጥይት ለሞት ተዳርገዋል፡፡ ባለፈው እሁድ ፕሬዚዳንቱ ባደረጉት ንግግር ግን የሟቾች ቁጥር 19 መሆኑን ነው የገለጹት፡፡

የኬንያ ዋነኛው የተቃዋሚ ፓርቲ ባለፉት ሳምንታት ለተከሰተው ሞት፣ የሩቶ መንግሥት ሃላፊነቱን እንዲወስድ በዛሬው ዕለት በሰጠው መግለጫ ጠይቋል፡፡

የኢኮኖሚ ባለሙያው ኬን ጊቺንጋ ለአሶሼትድ ፕሬስ በሰጡት ማብራሪያ፤ መንግሥት ኢኮኖሚው እንዲዳብር የሚያስችለውን የታክስ ማሻሻያ ለማድረግ የተለየ አቅጣጫ  መከተል አለበት፤ ብለዋል፡፡

በኬንያ ሥራ አጥነት በናጠጠበትና የኑሮ ውድነት በናረበት ሁኔታ፣ የፕሬዚዳንቱና ከፍተኛ ባለሥልጣኖቻቸው የተቀማጠለ ህይወት መምራት በህዝቡ ዘንድ ቁጣ መቀስቀሱን  ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡

ፕሬዚዳንቱ ላለፉት ሁለት ሳምንታት ተቃውሞ የቀሰቀሰውን የፋይናንስ ረቂቅ ህግ በፊርማቸው ባለማጽደቅ የኬንያውያኑን ጥያቄ የመለሱ ቢሆንም፣ ተቃዋሚዎች ግን በእርሳቸው ላይ እምነት እንደሌላቸው እየገለጹ  ነው - በምርጫ ቅስቀሳ ወቅት የገቡትን ቃል ያላከበሩ “ውሸታም መሪ” ናቸው በሚል፡፡ ለዚህም ነው “ሩቶ ከሥልጣን ይልቀቁ” የሚለው ድምጽ የበረታው፡፡

በሌላ በኩል፣ የኬንያ የአሁኑ ተቃውሞ በማህበራዊ ሚዲያ የተደራጀና መሪ- አልባ በመሆኑ ምክንያት፣ መንግሥት እንደ ወትሮው ሊቆጣጠረውና ሊያፍነው አዳግቶታል ነው የሚባለው፡፡ የወጣት ኬንያውያኑ ጥያቄ አሁን አንድና አንድ ብቻ ሆኗል - ”ፕሬዚዳንቱ ከሥልጣን ይልቀቁ“፡፡ የኬንያ ፕሬዚዳንት ከሥልጣን ይለቁ ይሆን? የኬንያ ተቃውሞስ እንዴት ነው የሚበርደውና ኬንያውያን ወደ ሰላማዊ ህይወታቸው የሚመለሱት? ለጊዜው ማንም መልስ ያለው አይመስልም፡፡


 “በጎ ፈቃደኝነት ድንበር፣ ወሰንና ዘር አያውቅም”



        ነገርን ከሥሩ ውሃን ከምንጩ እንዲሉ፣ በጎ ፈቃደኝነት ምንድን ነው? እንዴትስ ይገለጻል? በሚለው መሰረታዊ  ጥያቄ  የዛሬ ርዕሰ ጉዳያችንን  እንጀምር፡፡ እርግጥ ነው በጎ ፈቃደኝነት ለኢትዮጵያውያን አዲስ ጉዳይ አይደለም፡፡ ኢትዮጵያውያን በአገራቸው ብቻ ሳይሆን ባህር ማዶ ጭምር ተሻግረው የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ፈጽመዋል፡፡ ኮንጎና ኮሪያ ድረስ ዘምተው ዓለማቀፍ የበጎ ፈቃድ ተግባር  ተወጥተዋል፡፡
 በሌላ በኩል፣ በጎ ፈቃደኝነት ወይም በጎ አድራጎት የሚል መደበኛ ስም አይሰጠው እንጂ፣ በዕለት ተዕለት ህይወታችንም  ቢሆን  አንዱ ለሌላው በጎ እያደረገ ነው እዚህ የደረስነው፡፡ ሆኖም ዘመናዊነትና ግላዊነት ባሳደሩብን አሉታዊ ተጽዕኖ ሳቢያ፣ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ  ይህ ቱባ  እሴታችን እየተሸረሸረ መጥቷል፡፡ ለዚህም ነው ባለፉት ጥቂት ዓመታት፣ በመንግስት ደረጃ ጭምር፣ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ላይ ትኩረት ተደርጎ ሥራ  የተጀመረው፡፡ በእኒህ ዓመታት በተለይ በመዲናዋ የተከናወኑ የበጎ ፈቃድ ተግባራትን መቃኘት የዚህ ጽሁፍ ዓቢይ ዓላማ ነው፡፡   
ከዚያ በፊት ግን መነሻችን ላይ ያነሳነውን መሰረታዊ  ጥያቄ አስቀድመን እንመልስ፡፡ በጎ ፈቃደኝነት ምንድን ነው? እንዴትስ ይገለጻል? በጎ ፈቃደኝነት የራስን ጊዜ፣ አቅምና ችሎታ ወይም ሃብትና ክህሎት ሌላውን  ለማገዝ ወይም ሸክሙን ለማቅለል  የማዋል ተግባር ነው - በምላሹ ምንም ዓይነት ክፍያና ጥቅም ሳይፈልጉ፡፡ በሌላ አነጋገር፣ ለማህበረሰብ ወይም ለአገር በፈቃደኝነት ነጻ አገልግሎት መስጠት ብንለውም ያስኬዳል፡፡
የአዲስ አበባ አስተዳደር የህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን፣ ዋና ኮሚሽነር አቶ አብርሃም ታደሰ በበኩላቸው፤ “በጎ ፈቃደኝነት ማለት ሁሉም ሰው በራሱ ተነሳሽነትና ፍላጎት፣ ያለማንም አስገዳጅነት፣ በነጻ ፍላጎት ላይ ተመስርቶ፣ ያለምንም ክፍያ የሚሰጠው አገልግሎት ነው፡፡” ይላሉ፡፡ አክለውም፤ “በጎ ፈቃደኝነት ለሰዎች ጊዜህን፣ ገንዘብህንና ጉልበትህን በመስጠት ዘላቂ የሆነ የመንፈስ እርካታ የምታገኝበትና አብሮነትና ትብብርን ለማዳበር የሚያግዝ ተግባር ነው፡፡” በማለት ይገልጹታል፡፡
ከለውጡ ማግስት ጀምሮ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት በጠ/ሚኒስትር ዐቢይ መሃመድ ፊት አውራሪነት እየተለመደና እየተስፋፋ የመጣ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅትም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎችን የሚያሳትፍ ዘርፍ ሆኗል፡፡ በተለይ በመዲናዋ  ልዩ ትኩረት ተሰጥቶት ተቋማዊ በሆነ አሰራር እየተተገበረ ነው፡፡ በቅርቡ ይህንኑ ዘርፍ የሚመራ ተቋም በኮሚሽን ደረጃ ተዋቅሮ ወደ ሥራ መግባቱ ይታወቃል፡፡ የአዲስ አበባ አስተዳደር የህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን ዋና ተግባሩ ይሄው ነው፡፡
በነገራችን ላይ በዓለም  ላይ ለረዥም ዘመናት የዘለቀ ጠንካራ የበጎ ፈቃደኝነት ባህል ያላቸው በርካታ አገራት ይገኛሉ፡፡ እነ አሜሪካ፣ ካናዳ፣ አውስትራሊያ፣ እንግሊዝ፣ ኔዘርላንድና ስዊድን ይጠቀሳሉ፡፡ በወጉ የዳበረና የበለጸገ የበጎ ፈቃደኝነት ባህል እንዳላት በሚነገርላት አሜሪካ፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች  በተለያዩ የማህበረሰብ አገልግሎቶች ውስጥ  በንቃት እንደሚሳተፉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ እኒህ  አገራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎታቸውን ከራሳቸው አልፈው  ለሌሎችም ማድረስና ማዳረስ  ማዳረስ ችለዋል፤ ድንበር እየተሻገሩ፡፡  
በጎ ፈቃደኝነት ሌላው  ባህርይው - ወሰን፣ ድንበርና ዘር የማይገድበው መሆኑ ነው፡፡ የሰው ልጅ በመሆናችን ብቻ የተቸረን ጸጋ ነው፡፡ ስለዚህም የሰው ልጆች ባሉበት ሁሉ ይተገበራል፡፡ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ያለ ልዩነት የሚሳተፍበት ዘርፍም ነው፡፡ ከሕጻናት እስከ አረጋውያን፣ ከሊቅ እስከ ደቂቅ---ሁሉንም ያሳትፋል፡፡ በጎ ፈቃደኝነት እርዳታ አይደለም፤ ይልቁንም የፍቅርና አጋርነት መገለጫ ነው፡፡
መረጃዎች እንደሚጠቁሙት፤ ባለፉት አምስት ዓመታት፣ በመዲናዋ፣ በሰብአዊ፣ ማህበራዊና ሌሎች መርሃ ግብሮች አማካኝነት 22.7 ቢሊዮን ብር የሚገመት  የመንግስት ወጪ መሸፈን ተችሏል፡፡ በእኒህ ፕሮግራሞች በየዓመቱ በአማካይ ከ2 ሚሊዮን በላይ በጎ ፈቃደኞች የተሳተፉ ሲሆን፤ 900ሺህ ገደማ ነዋሪዎችም  ተጠቃሚ ሆነዋል፡፡
በአዲስ አበባ የሚከናወኑ  የበጎ ፈቃድ ተግባራት ዘርፈ ብዙ ናቸው፡፡ በተለይ በክረምት ወራት  የአቅመ ደካሞችና  አዛውንቶች  ቤትን  የማደስና የመገንባት ተግባር እየተስፋፋና እየተለመደ  መምጣቱን አለመመስከር ንፉግነት ነው፡፡ የዛሬ አምስት አመት ገደማ ጠ/ሚኒስትሩ የአንዲት አረጋዊት ቤት በማደስ ሀ ብለው ያስጀመሩት የበጎ ፈቃድ እንቅስቃሴ፣ ዛሬ ተስፋፍቶና ተጠናክሮ  በአቧሬና አካባቢዋ  አጀብ የሚያሰኝ ውጤት አስመዝግቧል፡፡ የበርካታ ነዋሪዎችን ህይወት በተጨባጭ  ለውጧል፡፡ በአካባቢው ባለ አስራ ሁለት ወለል የመኖሪያ  ሕንጻዎች ተገንብተዋል፡፡ የበጎ ፈቃደኝነት ትሩፋቱ ታዲያ በአቧሬ ብቻ ተወስኖ አልቀረም፡፡  ልደታ አካባቢ “የበጎነት መንደር” ተመስርቷል - በበጎ ፈቃድ አገልግሎት፡፡ በተመሳሳይ .በአራዳ፣ በቂርቆስ፣ በቦሌ፣ በየካ፣ በለሚ ኩራ፣ በንፋስ ስልክ፣ በኮልፌ፣ በአዲስ ከተማና በሌሎችም ...የአቅመ ደካማዎችና አረጋውያንን ቤቶች  የማደስና የመገንባት ተግባራት በስፋት ተከናውነዋል፡፡
በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ ለሚገኙ የህብረተሰብ ክፍሎች፣ ማዕድ ማጋራትም፣ ሌላው በስፋት እየተለመደ የመጣ የበጎ አድራጎት ተግባር  ነው፡፡  በዚህ ዓመት ብቻ ከ1.1 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ነዋሪዎች  ማዕድ የማጋራት ተግባር ተከናውኗል፡፡ በገንዘብ ሲሰላ ከ3.5 ቢሊዮን ብር በላይ የሚገመት ነው፡፡
የአዲስ አበባ አስተዳደር “አንድ ቤተሰብ ለአንድ ሰው” እና “አንድ ቤተሰብ ለአንድ ህፃን” በሚል በጀመራቸው መርሃ ግብሮች ቁጥራቸው ቀላል የማይባል አረጋውያንና ህጻናትን መደገፍ ተችሏል፡፡ የአዲስ አበባ አስተዳደር የህብረተሰብ ተሳትፎና በጎ ፈቃድ ማስተባበሪያ ኮሚሽን፣ ዋና ኮሚሽነር አቶ አብርሃም ታደሰ እንደሚናገሩት፤ ”ባለፈው ዓመት ከ24 ሺህ 500 በላይ የሕብረተሰብ ክፍሎች፣ በዚህ ትስስር ተቆራኝተው፣ ትናንት ለአገር ውለታ የከፈሉ አዛውንቶችን  እያገዙና  እየደገፉ ነው፡፡ ለአብነት ያህል፡- ”ታፍ ኢትዮጵያ“ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸው አርባ እናቶችን፣ ለሁለት ዓመት፣ በየወሩ አራት ሺህ ብር እየሰጠ በመደገፍ ላይ ይገኛል፡፡” ብለዋል፡፡
 “አንድ ቤተሰብ ለአንድ ሕጻን” በሚል መርሃ ግብርም፣ አንድ ባለሃብት 100 ሕጻናትን ከጨቅላነት እስከ ዩኒቨርስቲ ድረስ ለማስተማር መረከቡን የኮሚሽኑ ሃላፊ ገልጸዋል፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ባለሃብቱ መቶ ሕጻናትን ከእናቶቻቸው ሳይለዩ በየወሩ 3 ሺህ 500 ብር በመስጠት በእንክብካቤ ያድጋሉ፡፡ በባለሃብቱ ድጋፉ እስከ ዩኒቨርስቲ ትምህርት ድረስ የሚዘልቅ ነው፡፡ በተመሳሳይም 430 የሚሆኑ ሕጻናት በየክፍለ ከተማው እንዲሁ ድጋፍ እየተደረገላቸው ነው - ባለሃብቶች  ህጻናትን እየወሰዱ እያሳደጉ ነው፤ አረጋውያንን እየጦሩ እየደገፉ ነው፡፡
 እኒህ ሁሉ በመዲናዋ እየተካሄዱ ያሉ  የበጎ ፈቃደኝነት ትሩፋቶች ናቸው፡፡ ነዋሪዎች በሌላ በኩል በአረንጓዷ አሻራ መርሃ ግብር፣ ችግኝ በመትከል በንቃት ይሳተፋሉ፡፡ በጤናው ዘርፍ ደግሞ ነዋሪዎች ደም በመለገስ ለወገናቸው ይደርሳሉ፡፡ የመንግስትና የግል የጤና ተቋማት፣ እስከ ቀዶ ጥገና የሚደርስ ብዙ ወጪ የሚጠይቅ  ነጻ የህክምና አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡
ከዚህ አንጻር በመዲናዋ የሚከናወኑ የበጎ ፈቃደኝነት ተግባራት ድርብርብ የሆነ ትርፍ እንዳላቸው የሚናገሩት አቶ አብርሃም፤  የበጎ ፈቃደኝነት ተግባር የሃብት  ክፍፍልን በማረጋገጥ ረገድ ትልቅ ሚና እንደሚጫወት ይገልጻሉ፡፡  ከዚህ ሌላ “ትልቁ ሃብት” የሚባለው የወጣቶች ሰብዕና ግንባታ ላይ ያመጣው ለውጥ ነው ባይ ናቸው። ”ወጣቶች ለአካባቢያቸው፤ ለማሕበረሰባቸውና ለአገራቸው በነጻ መስራትና ማገልገል ሲለምዱ፣ አገር ወዳድ ትውልድ ይፈጠራል።” ብለዋል፡፡
የበጎ ፈቃደኝነት ትሩፋቶች ተቆጥረው አያልቁም፡፡  በነዋሪዎች መሃል የአንድነትና የትብብር ስሜት በመፍጠር የማህበረሰብ ግንኙነትን ያጠናክራል፡፡ በጎ ፈቃደኝነት ሙያዊ ዕድገትን ያዳብራል፡፡ በጎ ፈቃደኞች  በበጎ አድራጎት ተግባራት ሲሳተፉ፣ እግረ መንገዳቸውን አዳዲስ ክህሎቶችና ልምዶችን ይቀስማሉ፡፡ ይሄ ብቻ ግን አይደለም፡፡ በጎ ፈቃደኝነት ማህበራዊ ግንኙነትንም ያሰፋል፡፡ አዳዲስ ሰዎችን ለመተዋወቅ፣ ወዳጅነትን ለመመስረትና ማህበራዊ ትስስርን ለማስፋት ዕድሎችን ይፈጥራል፡፡ አስገራሚ ቢመስልም በጎ ፈቃደኝነት የጤና ትሩፋቶችም አሉት፡፡ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት፣ በጎ ፈቃደኝነት ውጥረትን በመቀነስ፣ ድባቴን በማስወገድና በአጠቃላይ የመንፈስ እርካታና  የደስታ ስሜትን በመጨመር የአዕምሮ ጤንነትን ያሻሽላል፡፡
መንግሥት በተደጋጋሚ እንደሚለው፣ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ በአገራችን እንደ ባህል እንዲዳብርና ጥቂቶች ብቻ ሳይሆኑ በርካታ ሚሊዮኖች የሚሳተፉበት ተግባር  ይሆን ዘንድ፣ በጽንሰ ሃሳቡ ዙሪያ ትርጉም ያለው  የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ ማከናወን ተገቢ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የአዲስ አበባ አስተዳደር፣ በየጊዜው የተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጥና ማስረጽ ተግባራትን እያከናወነ  ይገኛል፡፡  
በጎ ፈቃደኝነት፤ የማህበረሰብ አንድነትንና ትብብርን እንዲሁም ማህበረሰባዊ ለውጥን ለማምጣት ትልቅ መሳሪያ ነው፡፡ ትሩፋቱ ለብዙሃን የሚዳረስ ነው፡፡ በድፍን አገር ላይ  አዎንታዊ ተጽዕኖ ይፈጥራል፡፡
ባለፉት ጥቂት  ዓመታት፣ የበጎ ፈቃድ አገልግሎት፣ ከሌሎች የአገሪቱ አካባቢዎች በተሻለ መጠንና ፍጥነት  በመዲናዋ  እየተስፋፋ መጥቷል፡፡ ሌሎች የክልል መንግስታትና የከተማ አስተዳደሮችም የመዲናዋን አርአያነት በመከተል የበጎ ፈቃድ  አገልግሎትን ለማስፋፋትና ለማዳበር እየተጉ ይገኛሉ፡፡  
በመዲናችንም ሆነ በመላው አገሪቱ  የበጎ ፈቃደኝነት ጥረቶችንና ጅምሮችን በማበረታታትና በመደገፍ፣ ጠንካራና አይበገሬ ማህበረሰቦችን መገንባት እንዲሁም ለሁሉም  የምትመች ኢትዮጵያን መፍጠር የሁላችንም ሃላፊነት ነው፡፡ ክረምቱ ስኬታማ የበጎ ፈቃደኝነት ተግባራት የሚከናወንበት ይሁን!!

Page 4 of 714