Administrator

Administrator

  ‹‹…እኔ ትዳር በያዝኩ በሶስተኛው አመት የመጀመሪያ ልጄን አረገዝኩ፡፡ ከዚያም በአቅራቢያዬ ወደሚገኝ ሆስፒታል ሄድኩና ምርመራ መጀመር እንደምፈልግ ነገርኩዋቸው። እነርሱም ተቀብለውኝ ምርመራውን ስጀምር ባለቤቴን እንድጠራ ተነገረኝ፡፡ ለምንድነው? ብዬ ብጠይቅ መጀመሪያ ሁለታችሁም ደም ብትሰጡና ብትታዩ ጥሩ ነው፡፡ ተባልኩኝ፡፡ ከዚያም ወደቤት ተመልሼ የተባልኩትን ነገርኩና የተሰጠንን የጥሪ ወረቀት ስሰጠው…በድንገት ብድግ ብሎ በጥፊ መታኝ፡፡ ምንሆነህ ነው? ብዬ ስጠይቀው በወደቅሁበት በእርግጫ ደገመኝ፡፡ እንደምንም ተጥመልምዬ ከወደቅሁበት ተነሳሁኝ፡፡ እዛው ሄደሽ ጣጣሽን ጨርሺ፡፡ እኔ የምጠራበት ምን ምክንያት አለ? የሆንሽውን እዛው አያክሙሽም? እኔ ለምን እፈለጋለሁ? ብሎ ጮኸብኝ፡፡ ስንጯጯህ የሰሙ ሰዎች ገብተው ገላገሉንና በቀጣዩ ቀን ወደሆስፒታል አብረን ሄድን፡፡ ምርመራውንም የግድ አደረገ፡፡ ነገር ግን ሁለታችንም ቫይረሱ በደማችን ውስጥ የለብንም፡፡ እኔ ግን በዚያ ዱላ ምክንያት ታምሜ ጽንሱ ተቋረጠ፡፡ ጽንሱም ብቻ ሳይሆን ኑሮአችንም ፈረሰ፡፡ ምክንያቱም ቫይረሱ በደማችን ውስጥ ቢገኝ ኖሮ እንደሚገለኝ ከዚያው ከሆስፒታል ነግሮኝ ስለነበር ነው፡፡ እንደዚህ ያሉ ሰዎች አርቆ ማሰብ የተሳናቸውና በዘመኑ የሌሉ ሁዋላቀሮች ስለሆኑ ቢመከሩ ጥሩ ነው፡፡…››
ከላይ ያነበባችሁት ታሪክ በአምቦ ከተማ ቡና እያፈላች የምትተዳደር ወጣት ምስክርነት ነው፡፡ በአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል የማዋለጃ ክፍሉን የስራ እንቅስቃሴ ለመመልከት በስፍራው በተገኘንበት ጊዜ ጠበብ ባለ ቦታ ታካሚና አሳካሚ የሆኑ ሰዎች ሲጨናነቁ ተመልክተናል፡፡  ሁኔታውን ለመመልከት ዘልቀን መግባት ነበረብን፡፡ የነበረውን ሁኔታ እንዲያብራሩልን የህክምና ባለሙያዎችን አነጋግረናል፡፡ በቅድሚያ ያገኘናቸው በሱፈቃድ ባልቻ በአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል አዋላጅ ነርስ ናቸው፡፡
ጥ/    በሆስፒታሉ ለመታከም የሚመጡ ተገልጋዮች ከየት ከየት ናቸው?
መ/    በአምቦ ሆስፒታል የሚታከሙት የጽንስና ማህጸን ታካሚዎች የሚመጡት በአጠቃላይ በምእራብ ሸዋ ካሉት ወረዳዎች ካሉ ጤና ጣቢያዎችም ሆነ ሌሎች የህክምና ተቋማት ሲሆን ስፍራዎቹም ጉደር፤ ሸነን፤ ከሚባሉት እና በአብዛኛውም በግላቸው የሚመጡ ናቸው። በአብዛ ኛው የሚመጡት እናቶች ሕመምም በድንገት ጽንስ መቋረጥና እንዲሁም በተለያዩ ችግሮች ምክንያት ሕጉ በሚፈቅደው መሰረት ፈቅደው ጽንስ ለማቋረጥ የሚመጡም አሉ። ሆስፒታሉ በሪፈር ሕመምተኞችን የሚቀበልባቸው ተብሎ የተመደቡለት ጤና ጣቢያዎች ቢኖሩም በድንገተኛ የሚመጡት ግን ከየትኛውም አካበቢ  ወይንም በግላቸውም ቢሆን አይመለ ሱም፡፡ ምናልባት ሕክምናው የሚሰጥበት ስፍራ ቢጠብና ቢጨናነቅ እንኩዋን ሕይወትን ሳናተ ርፍ ወደሌላ ቦታ እንዲሄዱ አናደርግም፡፡ በእርግጥ ከአሁን ቀደም ሁሉ ነገር በዚሁ ሆስፒታል ብቻ ተጨናንቆ የሚሰጥ ሲሆን አሁን ግን ሌላ የሪፈራል ሆስፒታል ስለተከፈተ ከአቅም በላይ የሆኑትን ወደዚያ እንልካለን፡፡      
በመቀጠል ያነጋገርነው ማትያስ ለሜሳ አዋላጅ ነርስ የማዋለጃ ክፍሉ ኃላፊ ናቸው፡፡
ጥ/    የማዋለጃ ክፍሉ አቅም ምን ይመስላል?
መ/    ማዋለጃ ክፍሉ በጣም የሚጨናነቅ ጠባብ እና ውስን አልጋዎች ያሉት ነው፡፡ በእርግጥ የአምቦ ዩኒቨርስቲ ሪፈራል ሆስፒታል ከመጀመሩ በፊት እጅግ በጣም የሚጨናነቅ ነበር፡፡ በአሁኑ ወቅት ከጌዴዎ እና ከጉደር፤ ከጀልዱ አካባቢ ሪፈር የሚባሉት ወደ አምቦ ሪፈራል ሆስፒታል እንጂ እንደድሮው ወደ አምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል ባለመሆኑ መጨናነቁን ቀንሶታል፡፡ ነገር ግን አሁን ትንሽ ይሻላል ቢባልም ያው ችግሩ እንዳለ ነው፡፡ በአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል በአሀኑ ወቅት በወር የሚወልዱት እናቶች ወደ 178/አንድ መቶ ሰባ ስምንት የሚደርስ ሲሆን የአለው የአልጋ ቁጥር ግን 4/አራት እንዲሁም ኮች 4/አራት ብቻ ነው፡፡ በሆስፒታሉ ላይ ጫና የሚፈጥሩት በግላቸው ፈልገው የሚመጡት ታካሚዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ወላዶች በአብዛኛው ምንም የጤና ችግር የሌለባቸው እና በአቅራቢያቸው ባሉ የጤና ጣቢያዎች ሊወልዱ የሚችሉ ሆነው ሳለ ወደአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል በመምጣት የአልጋም ሆነ የባለሙያውን ኃይል እንዲጣበብ ያደርጉታል። ሆስፒታሉ ይበልጥ ከወሊድ ጋር በተያያዘ በሚፈጠሩ የጤና እክሎች በተቸገሩት ላይ ብቻ ቢያተኩርና ቢሰራ ጫናው ይቀንሳል የሚል እምነት አለ፡፡ ስለዚህም ጤነኛዎቹ ወላዶች እናት በምንም ሁኔታ ወደሆስፒታሉ ስትመጣ አንቺ ጤነኛ ወላድ ነሽና ተመለሽ እንደማይባል ስለሚያውቁ ብቻ  በሆስፒታሉ አሰራር ላይ ችግር ከማስከተል ቢቆጠቡ መልካም ነው፡፡
ጥ/    ወደሆስፒታሉ የሚመጡት እናቶች ይበልጡኑ የሚታዩባቸው ሕመሞች ምንድናቸው?
መ/    በሪፈርም ይሁን በግላቸው ወደሆስፒታሉ ለእርዳታ የሚመጡት እናቶች በአብዛኛው የሚታይባቸው ችግር በጤና ጣቢያም ይሁን በቤታቸው በረጅም ጊዜ ምጥ የተነሳ የማህጸን መፈንዳት እንዲሁም ከደም ግፊት ጋር በተያያዘ ኢክላምፕሲያ የመሳሰሉት በተጨማሪም ከወሊድ በሁዋላ የደም መፍሰስ ችግሮች ይገጥሙዋቸዋል፡፡ የማህጸን መፈንዳት ደርሶባቸው የሚመጡት በጽንሱ ላይ ጉዳት ደርሶ እናትየውንም ከሚያሰጋበት ደረጃ ላይ ሆነው ከሆስፒታል ሲደርሱ በከፍተኛ ርብርብ እናትየውን ለማዳን ሙከራ ይደረጋል፡፡
በመቀጠል ሀሳብዋን ያብራራችልን ነርስ ሲስተር ስንታየሁ አሰፋ ትባላለች፡፡ ሲስተር ስንታየሁ በእናቶችና በሕጻናት ጤና ላይ የምትሰራ ባለሙያ ነች፡፡
ጥ/  ከኤችአይቪ ጋር በተያያዘ ለእናቶች የሚሰጠው አገልግሎት ምን ይመስላል?
መ/    እናቶች በእርግዝናቸው ወቅት ለክትትል ሲመጡ አስቀድሞ የምክር አገልግሎት በመስጠት ምርመራ እንዲያደርጉ ደረጋል፡፡ ከአሁን ቀደም በሌላ ሆስፒታልም ይሁን በአምቦ አጠቃላይ ሆስፒታል ተመርምረው እራሳቸውን የሚያውቁ ቢሆንም እንኩዋን ከእርግዝናው ጋር በተያያዘ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ምክር እና አገልግሎቱን እንዲያገኙ የተቻለው ሁሉ ይደረጋል፡፡ ስለዚህም ቫይረሱ በደምዋ ውስጥ ያለባት አዲስ ተመርማሪ ስትገኝ ወዲያውኑ መድሀኒት እንድትጀምር ትደረጋለች፡፡ ቫይረሱ በደማቸው ውስጥ ያለባቸው እናቶች በሚወል ዱበት ጊዜ ወዲያውኑ Nevirapine የተሰኘውን መድሀኒት እንዲጀምሩ ይደረጋል፡፡  ከዚያም ሕጻናቱ በምንም መንገድ ቫይረሱ ከእና ታቸው እንዳይተላለፍባቸው ለማድረግ በሳይንሱ ረገድ የተቀመጠውን መስፈርት በሙሉ ለማሟላት ጥረት ይደረጋል፡፡
ጥ/    የትዳር ጉዋደኞች ስለሁኔታው ያላቸው ምላሽ ምንይመስላል?
መ/    ቀደም ሲል ቫይረሱ በደማቸው መኖሩን ያወቁ እናቶች ባሎቻቸውም ሁኔታውን የተረዱ በመሆኑ ምንም ችግር አይገጥምም፡፡ነገር ግን አዲስ ተመርማሪ ከሆነችና ቫይረሱ በደምዋ ውስጥ መኖሩን ገና ያወቀች ሴት ከሆነች ባለቤትዋን እንድትጠራ ወረቀት ይሰጣታል፡፡ ብዙዎቹ ባሎች ግን ወደሆስፒታል ለመቅረብ ፈቃደኛ አይሆኑም። አን ዳንዶቹም ቢመጡ እንኩዋን ተጣ ልተው አንዳንድ ጊዜ በሚስቶቻቸው ላይ ዱላ የሚ ሰነዝሩም አይጠፉ። ቢመጡም በትክክል ምር መራውን ለማድረግ ፈቃደኛ የማይ ሆኑበት አጋጣሚ ብዙ ነው፡፡ ውጤቱም አንዳንዴ ቫይረሱ በደማ ቸው የሚገኝ ሲሆን አንዳንዴ ደግሞ ወንዶቹ ቫይረሱ በደማቸው አይገኝም፡፡ በሆስፒታሉ በኩል ግን ሁለቱም ማለትም ባልና ሚስቱ ያሉበትን የጤና ሁኔታ አውቀው በወደፊት ሕይወታ ቸው ማድረግ ያለባቸውን ነገር ይመከራሉ፡፡  
አዋላጅ ነርስ በሱፈቃድ እንደሚገልጹት ወላድ እናቶችን በሚመለከት ያሉት መዘግየቶች አሁንም እንደሚንጸባረቁ ነው፡፡ አንዳንዶች ከመንገድ እርቀው ስለሚኖሩ ብዙ ጊዜ ምጥ ሲይዛቸው በፍጥነት ወደ ጤና ተቋም ለመሄድ ይቸገራሉ። ስለዚህም ከቤታቸው ወልደው ችግር ገጥሞአቸው ለሕክምናው ይመጣሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የአምቡላንስ አጠ ቃቀሙ ላይ ምናልባት ዘግይተው አምቡላንስ እንዲመጣ መጠየቅ ወይንም አምቡላንሶ ተጠርቶ በተለያዩ ምክንያቶች በፍጥነት አለመድረስ የመሳሰሉት ችግሮች እናቶቹን ወደሆስ ፒታል ከመምጣት ሊያዘገዩአቸው ይችላሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜ በደረሱበት ጤና ጣቢያም አገልግሎት አሰጣጡ ላይ አንዳንድ ችግሮች …ለምሳሌም እንግዴ ልጁን ማዋለድ አለመቻል የመሳሰሉት ችግሮች ገጥሞአቸው እናቶች ሪፈር ሊባሉ ይችላሉ፡፡ ስለዚህም ከእናቶች ጋር በተያያዘ አንድም ቸል ሊባል የሚገባው ነገር የለም፡፡ ለእናቶች የሚሰጠውን አገልግሎት በሚ መለከት ሁሉም ነገር ትኩረትን ይሻል፡፡


    የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና ከተማ በሆነችው ደባርቅ ከተማ የኪነ ጥበብ፣ የቱሪዝምና የኢንቨስትመንት ፎረም እንደሚካሄድ ተገለፀ፡፡ ከፎረሙ ጎን ለጎን ዘንድሮ ተማሪዎችን ተቀብሎ ማስተማር የጀመረው ደባርቅ ዩኒቨርሲቲም እንደሚመረቅ የዝግጅቱ አስተባባሪ ሀገሬ ሚዲያና ኮሚዩኒኬሽን ለአዲስ አድማስ አስታውቋል፡፡
በቅርቡ በተደረገው ድልድል የሰሜን ጎንደር ዞን ዋና ከተማ ደባርቅ፤ የአገራችን አስደናቂ ተራሮች ስነ ምህዳር መገኛ፣ የጥንታዊና ታሪካዊ መስህቦች ምድር ስትሆን፣ በዩኔስኮ የተመዘገበው ብቸኛው ፓርካችንን ጨምሮ በርካታ ተፈጥሯዊ፣ መንፈሳዊና ታሪካዊ መስህቦች ይገኙባታል። ፎረሙም ይህን ተፈጥሮ ይበልጥ ለማስተዋወቅና ምቹ የኢንቨስትመንት ሁኔታዎችን ለመፍጠር መዘጋጀቱም ተገልጿል፡፡
ከሚያዚያ 13-15 ቀን 2010 ዓ.ም በሶስቱ ቀናት ትልቅ የኪነ ጥበብ ትርኢት፣ በአስቸጋሪው የሊማሊሞ መንገድ ላይ ሩጫ እንዲሁም በዞኑ የተፈጥሮ ሀብቶች ዙሪያ ጥናታዊ ፅሁፎችና ውይይቶች የሚካሄዱ ሲሆን ታዋቂ የሙዚቃና የቴአትር አርቲስቶች የአካባቢው ተወላጅ ኢንቨስተሮች፣ ከፍተኛ የፌደራልና የክልል የመንግስት ባለሥልጣናት፣ ከአገር ውስጥና ከውጭ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በፎረሙ ላይ ይታደማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ሰሜን ጎንደርን ለማልማት በጋራ እንሩጥ” በሚል መርህ በሚዘጋጀው በዚህ ፎረም የሰሜን ጎንደር ዞን የአስተዳደር ህንፃ ግንባታ የመሰረት ድንጋይ ይቀመጣል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

Saturday, 14 April 2018 14:47

ጲላጦስ

  (የፍርደ ገምድሎች እንጦሮጦስ!)
        ይህን ሰው ስለ ምን ትከሱታላችሁ? አላቸው። (ዮሐ. 18፡29)
        በዚህ ሰው አንድ በደል ስንኳ አላገኘሁበትም አለ። (ሉቃስ 23፡4)

    (ካለፈው የቀጠለ)
3 - ዥዋዥዌ
በእርግጥም ጲላጦስ አለቅጥ እንዲንገጫገጭ ሆኖ ነበር...
  . . . አስቀድሞ ፤ (ዮሐ. 18፡31-32) . . . እናንተ ወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት አላቸው። አይሁድም ለእኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም አሉት፤ ኢየሱስ በምን ዓይነት ሞት ሊሞት እንዳለው ሲያመለክት የተናገረው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው። (ወንጀለኞችን በስቅላት ቅጣት መግደል ሮማዊያኑ ወደ ቅድስቲቱ ምድር ያመጡት አዲስ ባህል በመሆኑ፤ የኢትዮጵያ መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር - የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ 82 - ስቅለት - ነገር ግን እስራኤላውያን ሰውን በስቅላት አይገድሉም ነበር፤ ዘዳ 21፡21-23/ኢያሱ 10፡26)
በኋላም፤ ጲላጦስ ‹‹የአይሁድን ንጉሥ ልፈታላችሁ ትወዳላችሁን?›› ብሎ አማራጭ ሲያቀርብም፤ እግረ መንገድ አሁንም ከኢየሱስ ያጣውን ምላሽ ለማሟላትና ያንኑ ሮማዊያኑን የሚያባትታቸውን የንጉሥነቱን ጉዳይ ከሕዝቡም እያውጣጣ (investigate እያደረገ) ነበር፡፡ በተለይም በዮሐንስ ወንጌል እንደምናነበው፤ ጲላጦስ የኢየሱስን ፖለቲካዊ ‹አዝማሚያ› ለማወቅ አስልቶ ነበር ይላሉ፤ የታሪክ ተመራማሪያኑ፡፡ Pilate carefully questioned the prisoner about His political roll.
እውነትም ከዚያ ሁሉ ጥያቄና መልስ በኋላ አሁንም ለኢየሱስ ያንኑ ጥያቄ ደግሞ ያቀርብለታል . . .
ጲላጦስም፡- እንግዲያ ንጉሥ ነህን? አለው። ኢየሱስም መልሶ፦ እኔ ንጉሥ እንደ ሆንሁ አንተ ትላለህ። እኔ  ስለ እውነት ልመሰክር ስለዚህ ተወልጃለሁ ስለዚህም ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ከእውነት የሆነ ሁሉ ድምፄን ይሰማል አለው። ጲላጦስ፡- እውነት ምንድር ነው? አለው። (ምናልባት የጲላጦስ እውነት ንጉሡን ከማገልገል ያለፈ ስላልነበረ ይሆንን?) ይህንም ብሎ ዳግመኛ ወደ አይሁድ ወጥቶ እኔስ አንዲት በደል ስንኳ አላገኘሁበትም። ነገር ግን በፋሲካ አንድ ልፈታላችሁ ልማድ አላችሁ፤ እንግዲህ የአይሁድን ንጉሥ ልፈታላችሁ ትወዳላችሁን? አላቸው። ሁሉም ደግመው በርባንን እንጂ ይህን አይደለም እያሉ ጮኹ። በርባን ግን ወንበዴ ነበረ። (ዮሐ. 18፡37-40) እርሱም በፍርድ ወንበር ተቀምጦ ሳለ፣ ሚስቱ ስለ እርሱ ዛሬ በሕልም እጅግ መከራ ተቀብያለሁና በዚያ ጻድቅ ሰው ምንም አታድርግ ብላ ላከችበት። (ማቴ.27፡13-19) (ጲላጦስ ግን የሚስቱን ምክር አልሰማም፡፡ ሆኖም ግን አሁንም በኢየሱስ ላይ ለመፍረድ ዝግጁ አይደለምና ደግሞ ይጠይቃል) በርባንን ወይስ ክርስቶስ የተባለውን ኢየሱስን ማንኛውን ልፈታላችሁ ትወዳላችሁ? አላቸው፤ በቅንዓት አሳልፈው እንደ ሰጡት ያውቅ ነበርና። (ግን ይህን ራሱ የሚያውቀውንም ውስጡን አልሰማም)... በዚህ ሰው አንድ በደል ስንኳ አላገኘሁበትም አለ። (ሉቃስ 23፡4) ገዢውም፤ ምን ነው? ያደረገው ክፋት ምንድር ነው? አለ (ማቴ. 27፡23)
(እስከ መጨረሻው ቅጽበት ኢየሱስን ሊፈታው መፈለጉን እናስተውላለን፤ግና እርሱ ራሱ የወደደውንም አላደረገም፡፡ ወደ መጨረሻም ከከሳሾቹ ድምጽ ውስጥ ያስተጋባው አንዳች አስገምጋሚ ምላሽ ሳያናውጠው አልቀረም፡፡)
...ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎአልና አሉት። ስለዚህ ጲላጦስ ይህን ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ ፈራ፤ ተመልሶም ወደ ገዢው ግቢ ገባና ኢየሱስን አንተ ከወዴት ነህ? አለው። ኢየሱስ ግን አንድ እንኳ አልመለሰለትም። ስለዚህ ጲላጦስ አትነግረኝምን? ልሰቅልህ ሥልጣን እንዳለኝ ወይም ልፈታህ ሥልጣን እንዳለኝ አታውቅምን ? አለው። ኢየሱስም መልሶ፦ ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም፤ ስለዚህ ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ኃጢአቱ የባሰ ነው አለው። ከዚህ በኋላ ጲላጦስ ሊፈታው ፈለገ፤ ነገር ግን  . . . (ዮሐ. 19፡7-12)
(ፍፁም ባልጠበቀው መንገድ በስጋት የሚንጥና የሞት ፍርድ ውሳኔውን ከማሳለፍ ወዴትም ውልፍት ማለት የማያስችለው ወጥመድ ፊቱ ተደቀነበት! . . .)
...ይህንስ ብትፈታው የቄሣር ወዳጅ አይደለህም፤ ራሱን ንጉሥ የሚያደርግ ሁሉ የቄሣር ተቃዋሚ ነው እያሉ ጮኹ።
በርግጥም ያኔ፤ ጲላጦስ ክፉኛ ክው ያለ እናም በቃ በእጅጉ የተንገጫገጨ አሳዛኝ ሰው የሆነ ይመስላል፡፡ በደካማ ጎኑ ነበር የመጡበት፡፡ አዎን! ማንም ቢሆን በዚህ መሰል ሁኔታ ውስጥ ራሱን ቢያገኘው፤በዚያች ወሳኝ ፍትሀዊ የፍርድ ውሳኔ የማሳለፊያ ቁርጥ ጊዜ ላይ በፍርድ ወንበሩ ቢቀመጥ ላፍታም ቢሆን  ይዋልላል፡፡ ግን ደግሞ ሁለት አማራጭ ይኖረዋል፤ ወይ ከአለት የጸና የልዕለ ሰብዕና ካባ የሚያጎናጽፈውን እውነት ጠብቆ ለእውነቱና ለራሱ ህሊና ታማኝ መሆን ይችላል ወይም ደግሞ ህሊናውን እየቧጠጠ ለሚያደማ ሀሰት ተገዝቶ፣ የአዕምሮ እረፍቱን አሟጥጦ ደፍቶ፣ ሰላምና ክብሩን አጥቶ፣ እስከ ዘላለሙ ንፁህ ሰብእናውን አጉድፎ ከራሱ ከማንነቱና ከመላው ሕዋ ጋርም ተቆራርጦ ያርፈዋል። ውሳኔው ቀላል አይደለም፡፡ እናስ እሺ ጲላጦስ ምን ሊል ይችላል... ‹‹አሁን ባይኔ መጣሽ!››  እንዴ! ለምን ምንም ነገር ጥንቅር ብሎ አይቀርም፤የንጉሡን ወዳጅነት አጥቶ ከመኖር፡፡ ህእ!›› (‹‹የምኖረው ለማን ሆነና!›› አይነት፡፡)
...በዚህ አተያይ/ መላምት ዙሪያ ያጠነጠኑት የታሪክ ተመራማሪዎቹም ይህን አሻሚ የኢየሱስ ከሳሾች አቀራረብ፤ የጲላጦስን የዳኝነት አቋም እሁለት ቦታ የከፈለ (explicit threat against Pilate) ፈተና ነበር ይሉታል ፡፡
ጲላጦስ፤ በኢየሱስ ላይ ባሳለፈው ፍርዱም ለንጉሡ ስሞታ ቀርቦበት እንደለመደው ከምርመራ ጥያቄ ቢያመልጥም፤ በኋለኞቹ ተደጋጋሚ ስህተቶቹ ምክንያት ግን ወደ ሮማ መጠራቱ አልቀረለትም፡፡
4 - የፍርድ ጥፍር
‹‹ህማማት ነውና የይሁዳን ታሪክ ልንገርህ...›› ይለናል፤ የኔታ ስብሀት ለአብ ገብረ እግዚአብሔር በ567 ድርሰቱ ውስጥ አምስት ልጆቹንና ስድስተኛ ሚስቱን በረሀብ ሞት ተነጥቆ፣ 7ኛ አንድ እሱ ብቻውን ቀርቶ እብደት ባናወዘውና ታማኙን የእርሻ በሬውን አርዶ በመብላቱ ራሱን በአስቆሮቱ ይሁዳ በመሰለው ገጸ ባሕርይው አንደበት፡፡... ‹‹ ይሁዳ ከዳተኛ ነው ይላሉ፣ የኔን ታሪክ ያልሰሙ፡፡ ይሁዳ እንኳ ተጸጸተ፤ ተሰቀለ፤ ራሱን ገደለ፤ እኔ ግን! እኔ ግን! ወይኔ! ወይኔ! ወይኔ!
ይህ ድምጽ በሀገረ ገዢው፣ በተንገጫገጨው ዳኛ ልቦናም ውስጥ ያለማቋረጥ መጎሰሙ አይጠረጠርም፡፡
ጲላጦስ፤ ከቄሣሩ ጋር ሲገናኝ የቀረቡበትን ስሞታዎች ሁሉ በወዳጅነት መንፈስ ሊያስተባብል ይቻለዋልና እምብዛም አያሳስበውም፤ ምናልባትም በታማኝነትና ፍጹም ታዛዥነት ለአስር ዓመታት በጽናት ላበረከተው አገልግሎቱ ከንጉሡ ዘንድ ውዳሴና ሹመትም ሳይጠብቅ አይቀርም፡፡ አሳዛኙ ነገር ግን ጲላጦስ ሀገሩ ሲደርስ፤ እንዲያ አቅሉን እስኪስት ጠብ እርግፍ ያለለት ጌታው ጢባርዮስ ቄሣር ሞቶ ነበር። ይህም ብቻ አይደል፤ ጲላጦስ ገፍቶት/ ሰቅሎት የመጣው ክርስትናም ትንሣኤ አድርጎ በራሱም ምድር ዙሪያ ቀድሞት መድረሱንና ዘሩ ማጎንቆል መጀመሩን በገነገነ ጊዜ፤ (በጲላጦስ ፊት የካዳችሁትን ብላቴናውን ኢየሱስን አከበረው። ሐዋ.3፡13) በምርመራው ፍጻሜ በVienna-on-Rhone  በግዞት ሳለ ፤ ሁለመናውን እንደ ረመጥ እየፈጀ እሚያብከነክነው በኢየሱስ ላይ ያሳለፈው ፍርድ ሌት ተቀን እረፍት ስለነሳው፤  ጲላጦስም የከሀዲውን የይሁዳን ጽዋ ጨለጣት፡፡ ... ኢየሱስን አሳልፎ የሰጠው ይሁዳ እንደ ተፈረደበት አይቶ ተጸጸተ፥...ብሩንም በቤተ መቅደስ ጥሎ ሄደና ታንቆ ሞተ። (ማቴ. 27:3/5) ጲላጦስም እንዲሁ ‹‹የቤተ መንግሥት ክብሩን ጥሎ›› ራሱን ገደለ፡፡
ከቶ አይቀርም ሞቱ
ምንም ቢታክቱ
ምን ቢሰነብቱ፡፡
 (የሕዝብ ግጥም - በገና፡፡)
5 - ባርነት ወ ነጻነት
‹‹ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም።›› እንዲል መጽሐፍ፤ አልፋና ኦሜጋ ኗሪው ህያው ቃል፣ ስለ ፍጥረት ባርነት እና ስለ እግዚአብሔር ነጻነት፣ ክብር፣ተስፋ፣ ምህረት፣ ሕግ እና ፍርድ ...ያበረከተልንን የሕይወት ስንቅ አስታውሰን እናሳርግ ...ሰዎች ነንና ከኃጢዐት ፈተና ባናመልጥም፣ እንደ ስራችን ሳይሆን እንደ ፀጋና ቸርነቱ ማስተዋሉን ቢያድለን እንማርበት ዘንድ፤ ከልብ እውነቱ የተፋታ፣ ለሌሎች በባርነት ተኮድኩዶ፣ ላላመነበት እውነት አጎብድዶ ራሱን የካደ ሰው ያመሻሽ እድሜ ዘመን እርቃኑን ሲቀር ምን እንደሚመስል የምስኪኑ ፈራጅ አሳዛኝ ገድል ጥሩ ማሳያ ነውና ከጲላጦስ ከንቱ ፀፀት ያትርፈን፡፡ ሁሉ ከንቱ ከንቱ፡፡ እነሆ . . . (ሮሜ  8:20-21) ፍጥረት ለከንቱነት ተገዝቶአልና፥ በተስፋ ስላስገዛው ነው እንጂ በፈቃዱ አይደለም፤ ተስፋውም ፍጥረት ራሱ ደግሞ ከጥፋት ባርነት ነጻነት ወጥቶ ለእግዚአብሔር ልጆች ወደሚሆን ክብር ነጻነት እንዲደርስ ነው። (ገላትያ 5፡1) በነጻነት ልንኖር ክርስቶስ ነጻነት አወጣን፤ እንግዲህ ጸንታችሁ ቁሙ እንደ ገናም በባርነት ቀንበር አትያዙ። (የያዕቆብ መልእክት 2፡12-13) በነጻነት ሕግ ፍርድን ይቀበሉ ዘንድ እንዳላቸው ሰዎች እንዲህ ተናገሩ፥ እንዲህም አድርጉ። ምሕረትን ለማያደርግ ምሕረት የሌለበት ፍርድ ይሆናልና፤ ምሕረትም በፍርድ ላይ ይመካል።
አሜን ፡፡
መልካም ዳግማይ ትንሣኤ!!


    በአለማችን በተለያዩ መስኮች እጅግ ከፍተኛ ተወዳጅነትና ተደናቂነትን ያተረፉ ግለሰቦችን ዝርዝር በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው ዩጎቭ፣ ከሰሞኑም የ2018 ምርጦችን ይፋ ያደረገ ሲሆን የማይክሮሶፍቱ መስራች አሜሪካዊው ቢሊየነር ቢል ጌትስና ታዋቂዋ የሆሊውድ ተዋናይት አንጀሊና ጆሊ ቀዳሚነቱን ይዘዋል፡፡
ቢል ጌትስና አንጀሊና ጆሊ ላለፉት ሶስት ተከታታይ አመታት የአለማችን ቀዳሚዎቹ እጅግ ተወዳጅ ዝነኞች ሆነው መዝለቃቸውን የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፤ በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ በሁለቱም ጾታዎች 20 ሰዎች መካተታቸውንም አመልክቷል፡፡
ዩጎቭ ከ37 ሺህ በላይ ከሚሆኑ የ35 የአለማችን አገራት ዜጎች በድረገጽ በሰበሰበው የድምጽ አሰጣጥ መሰረት፤ በወንዶች ዘርፍ ከቢል ጌትስ ቀጥለው የአለማችን የአመቱ ተደናቂ የሆኑት የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ መሆናቸውንና ቻይናዊው የፊልም አክተር ጃኪ ቻን ሶስተኛ ደረጃን መያዙንም ጠቁሟል፡፡
የቢዝነስ ሰዎችና የስፖርቱ አለም ከዋክብት በበዙበት በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት መካከል ዋረን በፌ፣ ክርስቲያኖ ሮናልዶ፣ ሜሲና ዴቪድ ቤካም ይገኙበታል ያለው ዘገባው፤በፖለቲካው መስክ ከተመረጡት መካከልም የቻይናው ፕሬዚዳንት ዢ ጂፒንግ፣ ዶናልድ ትራምፕ እና ቭላድሚር ፑቲን እንደሚገኙበት አስታውቋል፡፡
የመዝናኛው መስክ ዝነኞች በብዛት በተካተቱበት በሴቶች ዘርፍ በአንጻሩ፣ የሁለተኛነትን ደረጃ የያዙት የቀድሞዋ የአሜሪካ ቀዳማዊት እመቤት ሚሼል ኦባማ ሲሆኑ ታዋቂዋ የቶክሾው አቅራቢ ኦፕራ ዊንፍሬይ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡
እስከ አስረኛ ባለው ደረጃ ውስጥ ከተካተቱት የአለማችን ሴቶች ውስጥ ቴለር ስዊፍት፣ ማዶና፣ ሂላሪ ክሊንተንና የጀርመን መራሂተ መንግስት አንጌላ መርኬል እንደሚገኙበትም ዘገባው ጠቁሟል፡፡

 የአሜሪካው ኩባንያ እጅግ ዘመናዊ እንደሆነ የተነገረለትን የጠፈር ላይ የቅንጦት ሆቴል በመክፈት፣ ለአንድ ምሽት 792 ሺህ ዶላር የመክፈል አቅም ላላቸው የናጠጡ ባለጸጎች አገልግሎት ሊሰጥ በዝግጅት ላይ  እንደሚገኝ ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡
ተቀማጭነቱን በሂውስተን ያደረገው ኦሪዮን ስፓን የተባለ ኩባንያ ከሶስት አመታት በኋላ በሚጀምረው በዚህ የቅንጦት የጠፈር ሆቴል ለመጀመሪያ ጊዜ አራት ደንበኞችን ለማስተናገድ ማሰቡን የዘገበው ብሉምበርግ፤ ደንበኞቹ በህዋው ሆቴል ለሚኖራቸው የ12 ቀናት ቆይታ እያንዳንዳቸው 9.5 ሚሊዮን ዶላር እንደሚከፍሉ አመልክቷል፡፡
ኩባንያው በሁለት የበረራ ባለሙያዎች በምትመራዋና 35 ጫማ በ14 ጫማ ስፋት ባላት መንኮራኩር ላይ በሚከፍተው በዚህ የጠፈር ላይ ዘመናዊ ሆቴል፤ የመክፈል አቅም ላላቸው ደንበኞች ከምድር በ200 ማይል ርቀት ላይ ከመሬት ስበት ውጭ ሆነው ለቀናት ሙሉ መስተንግዶ የሚያገኙበትን ዕድል ለመፍጠር ዝግጅቱን እያጧጧፈ እንደሚገኝ አስታውቋል፡፡
በአለማችን የጠፈር ቱሪዝም ታሪክ በግላቸው ከፍተኛ ገንዘብ በመክፈል ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ ጠፈር የተጓዙት አሜሪካዊው ባለሃብት ዴኒስ ቲቶ እንደነበሩ ያስታወሰው ዘገባው፤ ግለሰቡ በ2001 ወደ አለማቀፉ የጠፈር ማዕከል ላደረጉት ጉዞ 20 ሚሊዮን ዶላር ያህል መክፈላቸውንም ጠቁሟል፡፡

  በአለማችን 22 ሺ ያህል ሰዎች የሞት ፍርድ ይጠብቃቸዋል

    አለማቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም አምነስቲ ኢንተርናሽናል፤ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸውን ሰዎች በሞት በመቅጣትና በመግደል የምትታወቀው ቻይና፤ አሁንም ከአለማችን አገራት ቀዳሚነቱን መያዟን ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገው አመታዊ ሪፖርቱ አስታውቋል፡፡
ቻይና ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017 በሺህዎች በሚቆጠሩ ሰዎች ላይ የሞት ፍርድ ቅጣት ማስተላለፏን የጠቆመው የተቋሙ ሪፖርት፤ በአመቱ የገደለቻቸው ሰዎች ትክክለኛ ቁጥር ባይታወቅም በተቀረው አለም አገራት የተፈጸሙ ግድያዎች ተደምረው የቻይናን እንደማይደርሱ አመልክቷል፡፡
በአመቱ በርካታ ሰዎችን በሞት በመቅጣት በሪፖርቱ ከተጠቀሱ አገራት መካከል ኢራን፣ ሳኡዲ አረቢያ፣ ኢራቅና ፓኪስታን የሚገኙበት ሲሆን  በእነዚህ አገራት በድምሩ ከ830 በላይ ሰዎች በሞት መቀጣታቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡
በአመቱ የሞት ቅጣት ፍርድና ግድያ በመላወ ዓለም በተወሰነ ደረጃ መቀነስ ማሳየቱን ያስታወቀው የአምነስቲ ሪፖርት፤ በ2017 የፈረንጆች አመት ቻይናን ሳይጨምር በአለማችን 23 አገራት የሞት ቅጣት የተፈረደባቸው 993 ሰዎች መገደላቸውን አመልክቷል። በአለማችን በሚገኙ 53 አገራት፣ ምንም እንኳን በሁሉም ላይ ተፈጻሚ ባይደረግም በ2ሺህ 591 ሰዎች ላይ የሞት ፍርድ ተፈርዶባቸዋል ያለው ሪፖርቱ፤ በመላው አለም 22 ሺህ ያህል ሰዎች የሞት ፍርድ ይፈረድባቸዋል ተብሎ እንደሚጠበቅም አስታውቋል፡፡
ከሰሃራ በታች ባሉ አገራት ተስፋ ሰጪ ነገር መታየቱንና 20 ያህል የአካባቢው አገራት የሞት ፍርድ እንዲቀር መወሰናቸውን የጠቆመው ሪፖርቱ፤ አንዳንድ አገራት በአንጻሩ ከልክለውት የነበረውን የሞት ፍርድ ቅጣት በ2017 እንደገና ተግባራዊ ማድረግ መጀመራቸውን ጠቅሶ፤ከእነዚህም መካከል ባህሬን፣ ዮርዳኖስ፣ ኩዌትና የተባበሩት አረብ ኤሜሬትስ እንደሚገኙበት አስረድቷል፡፡

   የአለም የጤና ድርጅት ባለፈው ቅዳሜ በሶርያዋ ዱማ ከተማ በተፈጸመው ጥቃት የኬሚካል ጦር መሳሪያ ሰለባ በመሆን ለህመም የተዳረጉ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር 500 ያህል መድረሱን ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ድርጅቱ ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ፤ ህጻናትን ጨምሮ ለህመም የተዳረጉት 500 ያህል ሶርያውያን የመርዛማ ኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃት እንደተፈጸመባቸው የሚጠቁሙ የመተንፈሻ አካላትና የአእምሮ ስርዓት ችግር ምልክቶች እንዳሳዩ በሃኪሞች ተረጋግጧል ማለቱን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
የበሽር አልአሳድ መንግስት 70 ሰዎች ያህል ለህልፈተ ህይወት ተዳርገውበታል የተባለውን የምስራቃዊ ጉታ የኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃት አለመፈጸሙን በመግለጽ፤ አለማቀፍ ተቋማት ጉዳዩን እንዲያጣሩ የጠየቀ ሲሆን በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሶርያ አምባሳደር ሁሳም ኢዲን አላም በበኩላቸው፤ የአለም የጤና ድርጅት ይፋ ያደረገውን መረጃ፣ መሰረተ ቢስ ውንጀላ ነው ሲሉ ማጣጣላቸውን ዘገባው ጠቁሟል፡፡
በሶርያ የኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃት ሰለቦችን የማከምና የመንከባከብ ተልዕኮ የተሰጣቸው 800 የአገሪቱ የጤና ሰራተኞችን ማሰልጠኑን የጠቆመው የአለም የጤና ድርጅት፤ በምስራቃዊ ጉታ ጥቃት ለደረሰባቸው ለእነዚህ ዜጎች አፋጣኝ የህክምና እርዳታ ለመስጠት እንዲቻል የበሽር አል አሳድ መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርግ መጠየቁንም ዘገባው አመልክቷል፡፡ የበሽር አልአሳድ መንግስት የኬሚካል ጦር መሳሪያ ጥቃቱን አልፈጸምኩም ቢልም የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማርኮን በበኩላቸው፤ ጥቃቱን መፈጸሙን የሚያረጋግጥ ተጨባጭ መረጃ ማግኘታቸውን ከትናንት በስቲያ ገልጸዋል፡፡
ለጥቃቱ ሶርያንና ሩስያን ተጠያቂ ያደረጉት አሜሪካና እንግሊዝን ጨምሮ የተለያዩ የአውሮፓ አገራት መንግስታት፤ በመርዛማ ጋዝ ጥቃቱ ብዙዎችን ሰለባ አድርገዋል ባሏቸው የሶርያው ፕሬዚዳንት በሽር አል አሳድ ላይ ወታደራዊ እርምጃ መውሰድ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ በጋራና በተናጠል እየተወያዩ እንደሆነና የሩስያ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቃል አቀባይ በበኩላቸው፤ ወታደራዊ እርምጃው እንዳይወሰድ ማስጠንቃቃቸው ተዘግቧል፡፡

ጥንት በቀዝቃዛው ጦርነት ዘመን አንድ ምስኪን አሜሪካዊ፤ በአሜሪካኑ ሁዋይት ሐውስ ፊት ለፊት፣ ሣር ሲግጥ ይታያል፡፡ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ሰገነታቸው ላይ ቆመው ይህ ዜጋ ሳር ሲግጥ በማየታቸው እጅግ ተደንቀው ያስጠሩታል፡፡
ፕሬዚዳንት፤
“ምን ሆነህ ነው ሳር የምትግጠው?”
ምስኪኑ ዜጋም፤
“ርቦኝ፡፡ ጠኔ ሊገለኝ ሲሆን ሳርም ቢሆን ልቅመስ ብዬ ነው!”
ፕሬዚዳንት፤
“በል በቃህ፡፡ ለአምስት ዓመት በቀን ሶስት ጊዜ ማክዶናልድ (ሀምበርገር) በእኔ ሂሳብ ትበላለህ”፤ ግን ሥራ ፈልግ” ብለው አሰናበቱት፡፡ ተደስቶ ጮቤ እየረገጠ ሄደ፡፡
አምስት ዓመት በላ፡፡ አምስት ዓመት ጠገበ፡፡ ሥራ ግን አሁንም አላገኘም!
ስለዚህ ወደ ሩሲያ ሄደ፡፡ ሩሲያ ጥቂት እንደቆየ መራብ ጀመረ፡፡ ረሀቡን ለማስታገስ ወደ ዋናው የመንግሥት መናኸሪያ ወደ ክሬምሊን ሄደ፡፡ ከዚያም ፊት ለፊት ያገኘውን ሣር መጋጥ ጀመረ፡፡ የሩሲያው ፕሬዚዳንት ብሬዤኔቭ አዩት፡፡ ነገሩ ገርሟቸው አስጠሩት፡፡ በአጃቢ ገብቶ ፊታቸው ቀረበ፡፡ ብሬዥኔቭም፤
“ምን ሆነህ ነው እንዲህ እየተስገበገብክ ሳር የምትግጠው?” ሲሉ ጠየቁት፡፡
ምስኪኑ አሜሪካዊም፤
“ርሃብ! ጠኔ ሊገለኝ ነው ክቡር ፕሬዚዳንት!”
ፕሬዚዳንቱ ትንሽ አቅማሙና፤
“ታዲያ ለነገዬ አትችልም? ፕላንድ ኢኮኖሚ አታውቅም? በአንድ ቀን ግጠህ ልትጨርሰው ነው?” ብለው ኢኮኖሚያዊ ግሳፄ ሰጡት!!
*   *   *
አሜሪካኖች ሥራ ከመስጠት ይልቅ፤ ብር መስጠት ወደዱ፡፡ ሩሲያውያን በባዶ ሆድህ ቁጠባን ዕወቅ አሉ፡፡ ዓለም እንደዚያ ነበረች፡፡ ከዚያ ይሰውረን!
ለያዥ ለገራዥ ያስቸገረው የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ፤ ዛሬም በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ እንደሆነ አለ! የዓለም ባንክና የዓም አቀፍ የገንዘብ ድርጅት (አይኤምኤፍ) ዘገባዎች፤ (የአየለ አይኤምኤፍን ነብስ ይማር!) በኢትዮጵያ ኑሮና ካዝና አንፃር፡-
“ላም አለኝ በሰማይ
ወተቷንም አላይ” ናቸው፡፡ እንጂ እንደ  ካፒታሊስቶቹ ምኞትማ፡-
“ላም አለኝ በሰማይ
ወተቷ እሚከራይ!” በሆነ ነበር!
ከሁሉም ያውጣን!
“ገንዘቤን የወሰደ ሰው፣ ወሰደ እንበል ከንቱ ነገር የእኔም የሱም የዚያም ነበር
ግና ስሜን የሰረቀኝ የማያከብረውን ወስዶ፣ እኔን በግልፅ አደኸየኝ” (ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን)
ከማለት ሌላ ምን አቅም አለን፡፡
ካርል ማርክስ እንደሚለንም፤
“ፖለቲካ የኢኮኖሚ ጥርቅም መልክ ነው” (Politics is the concentrated form of economics)
ይህ እንግዲህ በሀገራችን ተሾመም፣ ተመረጠም፣ መሪ የሆነ ሰው፤ የፖለቲካም የኢኮኖሚም የአደራ ዕዳ እንዳለበት ነው፡፡ የህዝቡ ኑሮ እጅግ ጠያቂ ነው፡፡ ማንንም አይምርም! ይፈታተናል፡፡ ብልህ መሪ፤ አስተዋይ፣ ሆደ - ሰፊ፣ ትዕግሥቱን በብዛት የሰጣቸውን ባለ ራዕይ ጠቢባን የኢኮኖሚ ባለሙያዎችን በዙሪያው ሰብስቦ፡-
“ነገርን ከሥሩ
ውሃን ከጥሩ”
ማጤን ይጠበቅበታል!
“ጣሊያን ሊማሊሞን በመድፍ ሲደበድበው አደረ” ቢሉት፤
“ተወው ይበለው! እሱም መገተሩን አብዝቶት ነበር” አለ አሉ የጎንደር ሰው፡፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ግን በመድፍም ቢመታ ውልፊት አይልም! እንኳንስ በአንድ ጀምበር በአያሌ ጀምበሮችም የማይነቀነቅ ስለሆነ፣ “እንኳን ተለያይተን አንድ ሆነንም አስቸጋሪ ነው” ማለት ትክክለኛ አቅጣጫ ነው!
ተባብረን የኢኮኖሚያችንን ነገር ምን እናድርገው? እንባባል!
የቀድሞ፣ ቀድሞ መሪያችንን ራዕይ ብቻ የሙጥኝ በማለት አንወጣውም! ከአዳጊው ሁኔታ ጋር ምን ምን የኢኮኖሚ መንገድ እንቀይስ ካልተባባልን፣ የተሾመን የሚሽር፣ የመጣን የሚያወርድ አደጋ ፊታችን ላይ ተደቅኗል! እንደ ወትሮው፣
“ብቆጣም እመታሻለሁ፤ ብትቆጪም እመታሻለሁ” ዓይነት ዲሞክራሲ ዛሬ ወንዝ አያሻግርም! ደጋግመን “ፖለቲካው የኢኮኖሚው ጥርቅም መልክ ነው!” የሚለውን ጥልቅ አስተሳሰብ፤ በጥልቅ ግምገማም ቢሆን እንመርምረው!
ለክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች
መልካም የዳግማይ ትንሣዔ በዓል!

 ትዝ ይለኛል የዛሬ አስራ አራት አመት ነው፡፡ ከባለቤቴ ጋር አብረን ለመኖር ስወስን አንድ የቅርብ ወዳጄን ላገባ ነው ብዬ አማከርኩት፡፡ “እሱም ትዳር ጥሩ ነው፤ አግባ ግን ሪሞት ኮንትሮልህን አሳልፈህ እንዳትሰጥ” አለኝ፡፡ የመጀመሪያዎቹን ስድስት ወራት ሪሞት ኮንትሮሉን ላለመስጠት ብዙ ታገልኩ። ግን አልቻልኩም ፍቅር አሸነፈኝ፡፡ እናም ሪሞት ኮንትሮሉን አሳልፌ ሰጠሁ፡፡
ይህን በማድረጌ ግን ሦስት በዚህ ዓለም ላይ ካሉ ጥሩ ነገሮች ሁሉ አብልጬ እምወዳቸው ውብ ልጆች አተረፍኩ፡፡
ታዲያ ሁሌ የቴሌቪዥኔን ሪሞት ኮንትሮል ባየሁ ቁጥር፣ ያ ወዳጄ ትዝ ይለኛል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ አስባለሁ፤ አሁን እሳት ቢነሳ እማድነው ሪሞት ኮንትሮሉን ነው ወይስ ቴሌቪዥኑን? የሚቀለው ሪሞት ኮንትሮሉን ብድግ አድርጎ መሮጥ ነው፤ ግን ቴሌቪዥኑ ከሌለ ሪሞት ኮንትሮሉ ብቻውን ምን ይሰራል? ቢከብድም ቴሌቪዥኑን ማዳን ግን  ይጠቅማል፤ ምክንያቱም ቴሌቪዥኑ ከዳነ በኋላ ሪሞት ኮንትሮሉ በቀላሉ ስለሚገኝ፤ ባይገኝም  ቴሌቪዥኑ ምቾት ይቀንሳል እንጂ ያለ ሪሞት ኮንትሮል ማሳየት ስለሚችል! አሁን ሀገራችንን  እንደ ቴሌቪዥን፣ ስልጣንን ደግሞ እንደ ሪሞት ኮንትሮል እንይ፡፡
እሳት ሀገራችን ላይ ተነስቷል፡፡ እምናተርፈው ሪሞቱን ነው ወይስ ቴሌቪዥኑን? 180 አሁን ይህ ቁጥር ለሐገራችን ብዛትን መግለጫ ተራ ቁጥር አይደለም፡፡ ይህ ቁጥር ቀጣዩን የኢትዮጵያን እጣ ፈንታ የሚወስን ቁጥር ነው፡፡ እናንተ አንድ መቶ ሰማንያ ሰዎች!! ምናልባትም በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ ሀገራችሁ እጃችሁ ላይ ወድቃለች፡፡
ይህ ወቅት እንደ ሌላው ጊዜ እጅ አውጥታችሁና አጨብጭባችሁ የምትለዩት ወቅት አይደለም!! ይህ ወቅት እድሜ ልካችሁን በፀፀት ወይም በእርካታ የሚከተላችሁ ታሪካዊ ወቅት ነው!! እናም ተተኪውን ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ስትመርጡልን.........ስለ ብሄር ሳታስቡ.......በተፅእኖ ሳትረቱ.........ስለ ምቾታችሁ ሳትጨነቁ.......በሆዳችሁም በልባችሁም ሳይሆን በጭንቅላታችሁ ብቻ አስባችሁ........... ለወከላችሁ ብሔር ብቻ ሳይሆን ሳይፈልጉ እጃችሁ ስር ለወደቁ መላ ኢትዮጵያውያን ጭምር ተጨንቃችሁ፣ ይህቺን አገር ከገባችበት አዘቅት የሚያወጣት፤ ኢትዮጵያውያንን  ከዞረብን የዘረኝነት አባዜ የሚያላቅቀን፤ እያደር በጥልቀት ከምንሰምጥበት ያስተሣሠብ ድህነት የሚያድነን፤ ከዘወትር ተመፅዋችነት የምንገላገልበትን አቅጣጫ የሚያሣየን፤ መሪ ምረጡልን!ሪሞት ኮንትሮሉን ሳይሆን ቴሌቪዥኑን አድኑልን፡፡ ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን ይባርክ፡፡
(ከቴዎድሮስ ተሾመ ፌስቡክ)

 ትዝ ይለኛል የዛሬ አስራ አራት አመት ነው፡፡ ከባለቤቴ ጋር አብረን ለመኖር ስወስን አንድ የቅርብ ወዳጄን ላገባ ነው ብዬ አማከርኩት፡፡ “እሱም ትዳር ጥሩ ነው፤ አግባ ግን ሪሞት ኮንትሮልህን አሳልፈህ እንዳትሰጥ” አለኝ፡፡ የመጀመሪያዎቹን ስድስት ወራት ሪሞት ኮንትሮሉን ላለመስጠት ብዙ ታገልኩ። ግን አልቻልኩም ፍቅር አሸነፈኝ፡፡ እናም ሪሞት ኮንትሮሉን አሳልፌ ሰጠሁ፡፡
ይህን በማድረጌ ግን ሦስት በዚህ ዓለም ላይ ካሉ ጥሩ ነገሮች ሁሉ አብልጬ እምወዳቸው ውብ ልጆች አተረፍኩ፡፡
ታዲያ ሁሌ የቴሌቪዥኔን ሪሞት ኮንትሮል ባየሁ ቁጥር፣ ያ ወዳጄ ትዝ ይለኛል፡፡ አንዳንዴ ደግሞ አስባለሁ፤ አሁን እሳት ቢነሳ እማድነው ሪሞት ኮንትሮሉን ነው ወይስ ቴሌቪዥኑን? የሚቀለው ሪሞት ኮንትሮሉን ብድግ አድርጎ መሮጥ ነው፤ ግን ቴሌቪዥኑ ከሌለ ሪሞት ኮንትሮሉ ብቻውን ምን ይሰራል? ቢከብድም ቴሌቪዥኑን ማዳን ግን  ይጠቅማል፤ ምክንያቱም ቴሌቪዥኑ ከዳነ በኋላ ሪሞት ኮንትሮሉ በቀላሉ ስለሚገኝ፤ ባይገኝም  ቴሌቪዥኑ ምቾት ይቀንሳል እንጂ ያለ ሪሞት ኮንትሮል ማሳየት ስለሚችል! አሁን ሀገራችንን  እንደ ቴሌቪዥን፣ ስልጣንን ደግሞ እንደ ሪሞት ኮንትሮል እንይ፡፡
እሳት ሀገራችን ላይ ተነስቷል፡፡ እምናተርፈው ሪሞቱን ነው ወይስ ቴሌቪዥኑን? 180 አሁን ይህ ቁጥር ለሐገራችን ብዛትን መግለጫ ተራ ቁጥር አይደለም፡፡ ይህ ቁጥር ቀጣዩን የኢትዮጵያን እጣ ፈንታ የሚወስን ቁጥር ነው፡፡ እናንተ አንድ መቶ ሰማንያ ሰዎች!! ምናልባትም በታሪካችን ለመጀመሪያ ጊዜ ሀገራችሁ እጃችሁ ላይ ወድቃለች፡፡
ይህ ወቅት እንደ ሌላው ጊዜ እጅ አውጥታችሁና አጨብጭባችሁ የምትለዩት ወቅት አይደለም!! ይህ ወቅት እድሜ ልካችሁን በፀፀት ወይም በእርካታ የሚከተላችሁ ታሪካዊ ወቅት ነው!! እናም ተተኪውን ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ስትመርጡልን.........ስለ ብሄር ሳታስቡ.......በተፅእኖ ሳትረቱ.........ስለ ምቾታችሁ ሳትጨነቁ.......በሆዳችሁም በልባችሁም ሳይሆን በጭንቅላታችሁ ብቻ አስባችሁ........... ለወከላችሁ ብሔር ብቻ ሳይሆን ሳይፈልጉ እጃችሁ ስር ለወደቁ መላ ኢትዮጵያውያን ጭምር ተጨንቃችሁ፣ ይህቺን አገር ከገባችበት አዘቅት የሚያወጣት፤ ኢትዮጵያውያንን  ከዞረብን የዘረኝነት አባዜ የሚያላቅቀን፤ እያደር በጥልቀት ከምንሰምጥበት ያስተሣሠብ ድህነት የሚያድነን፤ ከዘወትር ተመፅዋችነት የምንገላገልበትን አቅጣጫ የሚያሣየን፤ መሪ ምረጡልን!ሪሞት ኮንትሮሉን ሳይሆን ቴሌቪዥኑን አድኑልን፡፡ ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ህዝቦቿን ይባርክ፡፡
(ከቴዎድሮስ ተሾመ ፌስቡክ)