Administrator

Administrator

     መንግስት በአጠቃላይ ከ725 ሚሊዮን ብር በላይ ድጎማ በማድረግ ሰርቻቸዋለሁ ያላቸው 972 የ40/60 መኖሪያ ቤቶች  እጣ ዛሬ ከቀኑ 7 ሰዓት ላይ የሚወጣ ሲሆን ዕድለኞች በወር ውስጥ ቤታቸውን ይረከባሉ ተብሏል፡፡  
ዛሬ ለእጣ ከተዘጋጁት 972 ቤቶች የሚጠበቅባቸውን የቤት ዋጋ ሙሉ ለሙሉ የከፈሉ 11 ሺህ 88 ቤት ፈላጊዎች የሚወዳደሩ ሲሆን ከነዚህ እድለኞች ውስጥ 20 በመቶ ለመንግስት ሰራተኞች፣ 3 በመቶ (29 ቤቶች) ለዳያስፖራዎች ቅድሚያ እድል የሚሰጥባቸው ይሆናሉ፡፡
የቤቶቹን እጣ አወጣጥ አስመልክቶ ከትናንት በስቲያ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ የከተማ አስተዳደሩ፣ የኮንስትራክሽን ሚኒስቴርና ቤቶች ልማት ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡ ሲሆን ለእነዚህ ግንባታቸው ከተጀመረ ከ4 ዓመት በኋላ ለተጠናቀቁ 972 ቤቶች አጠቃላይ ወጪ፣ ቤት ፈላጊዎች ከቆጠቡት በተጨማሪ መንግስት ከ725 ሚሊዮን ብር በላይ ድጎማ አድርጎባቸዋል ተብሏል፡፡
የ40/60 የቤት ፕሮግራም ከ4 ዓመት በፊት 44 ሲደረግ ባለ 1 መኝታ ቤት 55 ካሬ ሜትር፣ ባለ 2 መኝታ 75 ካ.ሜ እንዲሁም ባለ 3 መኝታ 100 ካ.ሜትር ስፋት እንዲኖራቸው ታቅዶ የነበረ ቢሆንም ኋላ ላይ በተደረገ የዲዛይን ማሻሻያ ባለ 1 መኝታ ቤት እንዳይኖር ተደርጎ፣ ባለ 1 የነበረው ወደ ባለ 2 መኝታ ቤት 125 ካ.ሜትር ስፋት፣ ባለ 2 የነበረው ወደ ባለ 3 መኝታ ከፍ ተደርጎ፣ በ150 ካ.ሜትር ላይ እንዲሁም ባለ 3 የነበረው ወደ ባለ 4 መኝታ ቤት ከፍ ተደርጎ፣ 168 ካ.ሜትር ስፋት እንዲኖራቸው መደረጉ ተገልጿል፡፡  
የቤቶቹ ዋጋም ቀደም ሲል በካሬ ሜትር በ3200 ብር ታስቦ የነበረው ወደ 5680 ብር ከፍ ማለቱን፣ መንግስት በእያንዳንዱ ካሬ ሜትር ላይ የ720 ብር ድጎማ አድርጎ፣ እድለኞች ቤቱን በካሬ ሜትር 4918 ብር ሂሳብ እንዲረከቡ ማመቻቸቱን በመግለጫው ተጠቁሟል፡፡ በዚህም መሰረት፤ ዛሬ እጣ የሚወጣባቸው መኖሪያ ቤቶች ላይ እያንዳንዱ ባለ እድለኛ ቀድሞ ከነበረው ዋጋ ላይ በካሬ ሜትር 1718 ብር ጭማሪ እንደሚከፍል ታውቋል፡፡
በቤቶቹ ዋጋ ላይ በጠቅላላው 170 ሚሊዮን ብር ድጎማ መደረጉን እንዲሁም አስተዳደሩ ፓርኪንግ ለመሳሰሉ ወጪዎች 140 ሚሊዮን፣ ለእሳትና ድንገተኛ አደጋዎች መከላከያ 97 ሚሊዮን እና ለቫት 168 ሚሊዮን የከፈለውን ጨምሮ 725 ሚሊዮን ብር ድጎማ ማድረጉ ተመልክቷል፡፡
ለመኖሪያ ቤትነት እጣ ከሚወጣባቸው ቤቶች በተጨማሪ 320 የንግድ ቤቶችም በእለቱ በመነሻ ዋጋ በካሬ ሜትር 172 ሺህ ብር ለጨረታ ይቀርባሉ ተብሏል፡፡ ከ40/60 ቤቶች የተወሰኑት ለመንግስት ቤቶች ኤጀንሲ እንዲሰጥ ጥያቄ መቅረቡን የጠቆሙት የአስተዳደሩ ም/ከንቲባ አቶ አባተ ስጦታው፤ዕድለኞች ክፍያ ፈፅሞ ቤቶቹን ለመውሰድ የሚከብዳቸው ከሆነ መንግስት ራሱ ቤቱን ይገዛዋል፤ዋጋው አሁን በዝቶብኛል ያሉ በቀጣይ በሚወጡ እጣዎች የመካተት እድል ይኖራቸዋል ብለዋል፡፡  
የንግድ ባንክ ፕሬዚዳንት አቶ በቃሉ ዘለቀ በበኩላቸው፤ ዛሬ እጣ የሚወጣባቸው የክራውንና የሠንጋ ተራ ሳይት ቤቶች መሠረተ ልማት እንደተሟላላቸውና በጥራት መሰራታቸውን ሙሉ ለሙ አረጋግጦ ባንኩ መረከቡን አስታውቀዋል፡፡
በአጠቃላይ በ40/60 የቤቶች ፕሮግራም በ2005 ዓ.ም 164 ሺህ ያህል ቤት ፈላጊዎች ተመዝግበው የነበረ ሲሆን በአሁኑ ወቅት 140 ሺህ ቤት ፈላጊዎች ቁጠባቸውን ሳያቋርጡ አድላቸውን እየተጠባበቁ ነው ተብሏል፡፡ በቀጣይ ዓመትም 20 ሺህ ቤቶችን ለተመዝጋቢዎች ለማስተላለፍ እቅድ መያዙን የስራ ሃላፊዎቹ አብራርተዋል፡፡

  የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ድንጋጌዎች በመተላለፍ ህገ መንግስታዊ ስርአቱን በኃይል ለማስወገድ ተንቀሳቅሰዋል በሚል የተከሰሱት አንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ የምስክሮችን ዝርዝር የማወቅ መብትን” በተመለከተ ያቀረቡት የክስ መቃወሚያ ላይ የፌዴሬሽን ም/ቤት የህግ ትርጉም እንዲሰጥበት ፍ/ቤቱ ብይን ሰጠ፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና ለፍ/ቤቱ ካቀረቧቸው የክስ መቃወሚያዎች መካከል ‹‹ክሱ የተሟላ አይደለም፤ ክሱ ፖለቲካዊ ነው፤ በሽብር ክስ ሳልከሰስ የሽብር ክስ ማስረጃ ሊጠቀስብኝ አይገባም›› የሚሉና ሌሎች የክስ መቃወሚያ በጠበቆቻቸው በኩል ያቀረቡ ቢሆንም ከአንዱ በስተቀር ቀሪዎቹን መቃወሚያዎች ፍ/ቤቱ ትናንት በዋለው ችሎት እንዳልተቀበላቸው አስታውቋል፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና የተከሰሱት በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የማስፈፀሚያ ደንብና በወንጀለኛ መቅጫ ህግ አንቀፅ ነው፡፡ የማስረጃ ዝርዝሩ የቀረበበባቸው ደግሞ በፀረ ሽብር አዋጁ መሰረት መሆኑን የዶ/ር መረራ የህግ አማካሪና ጠበቃ አቶ ወንድሙ ኢብሣ ለአዲስ አድማስ አስረድተዋል፡፡ በሽብር የተከሰሰ ሰው፤ የሰው ምስክሮች ላይገለጡለት እንደሚችል በህግ ተደንግጓል፡፡
ተከሳሹ በሽብር ወንጀል አለመከሰሳቸውን በመጥቀስ የሰው ማስረጃ ዝርዝሮች እንዲገለጥላቸው ጥያቄ በማቅረባቸው ፍ/ቤቱ የህግ ትርጉም ያስፈልገዋል ሲል ፌዴሬሽን ም/ቤት የህግ ትርጉም እንዲሰጥበት ብይን ሊሰጥ መቻሉን አቶ ወንድሙ አብራርተዋል፡፡
የፌዴሬሽን ም/ቤትን የህግ ትርጉም ለመጠባበቅ ጉዳዩ ለሐምሌ 25 ቀን 2009 ዓ.ም ተቀጥሯል፡፡
ዶ/ር መረራ ፍ/ቤት የመናገር እድል እንዲሰጣቸው ጠይቀው ባደረጉት ንግግር፤ “የኔ ክስ የፖለቲካዊ ክስ ነው፣ ለኦሮሞ ህዝብ መብት በመታገሌ ነው የተከሰስኩት፣ ለመላ የኢትዮጵያ ህዝቦች ነፃነት በመቆሜ ነው፤ ለሃቀኛ ፌደራል ስርአት መገንባትና ነፃ ፍ/ቤት፣ ነፃ የዳኝነትና የፍትህ ስርአት እንዲፈጠር ስለታገልኩ ነው የተከሰስኩት፡፡
ይሄን ትግል እኔ ብቻ አይደለሁም የታገልኩት፤ ቀደም ሲል አቤ ጉበኛ የሚባል ደራሲ “አልወለድም” የሚል መፅሃፍ ፅፎ ለንጉሡ ማስጠንቀቂያ ነግሮ፣ ንጉሡ ሳይሰማቸው መጨረሻው እንደዛ ሆነ፤ በደርግ ስርአት ደግሞ በአሉ ግርማ “ኦሮማይ” የሚል መፅሐፍ ፅፎ ለደርግ መንግስት ምክር ቢሰጥ ሳይሰማ ቀርቶ የሆነውን ታሪክም ፍ/ቤቱም ያውቃል፤ እኔ ደግሞ “የተራበ ህዝብ መሪዎቹን ይበላል” ብዬ መፅሓፍ ፅፌያለሁ፤ እባካችሁ ዳኞች ለታሪክ ስትሉ እነዚህን ሶስት መፅሃፎች አንብቡ …. የሰራሁት ወንጀል የለም፡፡ ለሁላችንም የምትሆን ህግና የህግ የበላይነት የሰፈነባት ሰው ሁሉ በእኩል የሚኖርባትን ሀገር እንመስርት ብዬ አንድ ለሆዱ ከሚያስብ ምሁር በላይ ዋጋ በመክፈሌ ነው የተከሰስኩት” ማለታቸው ታውቋል፡፡






 የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት በአህጉራዊ ደረጃ ለሚደረጉ ውድድሮች በሚኖረው  የማጣርያ ግጥሚያዎች ተሳትፎ  በቂ ትኩረት ያስፈልገዋል፡፡ በ2019 የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታቸው ከሁለት ሳምንት በፊት በአክራ ከተማ 5ለ0 ከባድ ሽንፈት የገጠማቸው ዋልያዎቹ ይህ ደካማ አጀማመራቸው ብዙዎችን አላስደሰተም፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ወደ አፍሪካ ዋንጫው የምድብ ማጣርያ የሚመለሰው ከ8 ወራት በኋላ እንደሆነ ይታወቃል፡፡
በሌላ በኩል በ2018 እ.ኤ.አ ኬንያ ለምታዘጋጀው 5ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ቻን 2ኛ ዙር ማጣርያ ሰሞኑን ዝግጅታቸውን የሚቀጥሉ ይሆናል፡፡ በቻን 2ኛ ዙር ማጣርያ የመጀመሪያው ጨዋታ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከሜዳ ውጭ የሚገናኘው ከጅቡቲ አቻው ጋር ነው፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና  አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ በቻን  ከጅቡቲ ጋር ከሜዳ ውጭ ለሚገናኙበት  የ2ኛ ዙር ማጣርያ ጨዋታ  ዝግጅት   አዳዲስ ተጫዋቾችን ጠርተዋል፡፡ ዋና አሰልጣኙ በአገር ውስጥ የሊግ ተጨዋቾች የተደራጀ ስብስባቸውን ይዘው  ለዝግጅት   ወደ ድሬዳዋ እንደሚያመሩ ይጠበቃል፡፡በ2018 እ.ኤ.አ ኬንያ ለምታስተናግደው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ የምስራቅና መካከለኛው አፍሪካ ኮታ ለ3 አገራት ነው። ኬንያ በአዘጋጅነቷ በቀጥታ ማለፋን ያረጋገጠች ሲሆን ሌሎች 2 ብሔራዊ ቡድኖች በ2ኛ እና 3ኛ ዙር በሚካሄድ ቅድመ ማጣሪያዎች የሚወሰኑ ይሆናል፡፡ ከ2 ሳምንታት በኋላ በሚቀጥለው የሁለተኛ ዙር ማጣሪያ ደቡብ ሱዳን ከኡጋንዳ፤ ጅቡቲ ከኢትዮጵያ፣ ታንዛኒያ ከሩዋንዳ እንዲሁም ብሩንዲ ከሱዳን ይገናኛሉ፡፡
ለቻን 2018 ማጣርያ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የተጫዋቾች ዝርዝር
ግብ ጠባቂዎች
ጀማል ጣሰው (ጅማ አባ ቡና)፣ ሳምሶን አሰፋ (ድሬዳዋ ከተማ) ፣ ለአለም ብርሃኑ (ሲዳማ ቡና)
ተከላካዮች
አስቻለው ታመነ (ቅዱስ ጊዮርጊስ) ፣ ሳላዲን በርጌቾ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)፣ አብዱልከሪም መሃመድ (ኢትዮጵያ ቡና)፣ አንተነህ ተስፋዬ (ሲዳማ ቡና)፣ ሙጂብ ቃሲም (አዳማ ከተማ)፣ ስዩም ተስፋዬ (ደደቢት) ፣ ደስታ ዮሀንስ (ሀዋሳ ከተማ)፣ አምሳሉ ጥላሁን (ፋሲል ከተማ)
አማካዮች
ሽመክት ጉግሳ (ደደቢት)፣ ሙሉአለም መስፍን (ሲዳማ ቡና)፣ ጋዲሳ መብራቴ (ሃዋሳ ከተማ) ፣ ታፈሰ ሰለሞን (ሀዋሳ ከተማ) ፣ ምንተስኖት አዳነ (ቅዱስ ጊዮርጊስ) ፣ ናትናኤል ዘለቀ (ቅዱስ ጊዮርጊስ) ፣ በኃይሉ አሰፋ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)
አጥቂዎች
ጌታነህ ከበደ (ደደቢት)፣ አዲስ ግደይ (ሲዳማ ቡና)፣ አብዱልራህማን ሙባረክ (ፋሲል ከተማ)፣ ሳላዲን ሰዒድ (ቅዱስ ጊዮርጊስ)
በ2019 እኤአ ላይ ካሜሮን ለምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ  በተጀመረው የምድብ ማጣርያ በምድብ 6 ጋና በአክራ ኢትዮጵያን 5ለ0 ስታሸንፍ ሴራሊዮን በሜዳዋ ኬንያን 2ለ1 ረታለች፡፡
ሴራሊዮን በዋና ከተማዋ ፍሪታውን በሚገኘው ብሄራዊ ስታድዬም ኬንያን 2ለ1 ስታሸንፍ ዋሌይ በ22ኛው ደቂቃ ላይ እንዲሁም አምበሉ ባንጉራ በ69ኛው ደቂቃ ላይ በፍፁም ቅጣት ምት ባስቆጠሯቸው ጎሎች ነው፡፡ የኬንያን ብቸኛ ግብ ያስቆጠረው ኦሉንጋ በ75ኛው ደቂቃ ላይ ነበር፡፡ ሴራሊዮን ኬንያን በሜዳዋ በማሸነፍ ያሳየችው ጅማሮ ለብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋቾች ከፍተኛ መነቃቃት ፈጥሮላቸዋል፡፡ ሎን ስታርስ የሚባለው ብሄራዊ ቡድኑን በአምበልነት የሚመራው ባንጉራ ለቢቢሲ በሰጠው አስተያየት ለማንም የማንመለስ ጠንካራ ቡድን ነን ሲል ተናግሯል፡፡ ሴራሊዮን በአፍሪካ ዋንጫ ለ2 ጊዜያት የተሳተፈችው በ1994 እና 1996 እኤአ ላይ ነበር፡፡ በሰኔ ወር የፊፋ ወርሃዊ የዓለም እግር ኳስ ደረጃ በ309 ነጥብ 113ኛ ላይ ትገኛለች፡፡  የተጨዋቾች ስብስቧ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 3.63 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡ በተያያዘ የኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን  በሴራሊዮን ለደረሰው ሽንፈት ምቹ ባልሆነ ስታድዬም ጨዋታ መደረጉ እንዲሁም የዳኝነት በደል መብዛቱን ምክንያት አድርገዋል፡፡ ይህን አስመልክቶም ለአፍሪካ የእግር ኳስ ፌደሬሽን የክስ ማመልከቻ ማስገባታቸው ታውቋል፡፡ በተጨማሪም የአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣርያውን የሃራምቤ ኮከቦች በሽንፈት መጀመራቸው በፌደሬሽኑ አካባቢ የነበረው የአስተዳደር ቀውስ ቆስቁሶታል፡፡ በተለይ ከ2018 የቻን ውድድር አዘጋጅነት በተያያዘ ነው፡፡ የኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ከመንግስት ሙሉ ድጋፍ ባለማግኘቱ መስተንግዶው ማቀላጠፍ አልቻልኩም በሚል እያማረረ ነው፡፡ የካፍ ኮሚቴ ሰሞኑን በናይሮቢ በነበረው ጉብኝት በ2018 እኤአ የሚካሄደው 5ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ሊጀመር 6 ወራት ቢቀሩትም ኬንያ ሙሉ ለሙሉ ዝግጁ አለመሆኗን በመጥቀስ፤ ሌላ አስተናጋጅ በሚመርጥበት ሁለተኛ ዕቅድ እየሰራ መሆኑን አስታውቋል፡፡ በ2020 እኤአ 6ኛውን ቻን እንድታዘጋጅ የተመረጠችው ኢትዮጵያ፤ እንዲሁም ሞሮኮና ኮትዲቯር በምትክነት መስተንግዶውን ለመረከብ ፍላጎት አላቸው። ኬንያ በአፍሪካ ዋንጫ ለአምስት ጊዜያት የተሳተፈችው በ1972፤ በ1988፤ በ1990፤ በ1992 እና በ2004 እኤአ ላይ ነበር፡፡ በሰኔ ወር የፊፋ ወርሃዊ የዓለም እግር ኳስ ደረጃ በ463 ነጥብ 74ኛ ላይ የምትገኝ ሲሆን ስብስቧ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 17.06 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡
ከምድብ 6 የምድብ ማጣርያውን ለማለፍ ቅድሚያ ግምት የተሰጣት ጋና በአክራ ከተማ በፍፁም የጨዋታ ብልጫ ኢትዮጵያን 5ለ0 ማሸነፏ ብዙዎችን አላስደነቀም። ለጥቋቁሮቹ ክዋክብቶች ጎሎቹን በ10ኛው ደቂቃ ላይ አሳሞሃ ጊያን፤ በ15ኛው ደቂቃ ቦዬ፤ በ35ኛው ደቂቃ ኦፍሪ እንዲሁም ድዋሜና በ48ኛው እና በ70ኛው ደቂቃዎች ላይ አስመዘግበዋል፡፡ የጋና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ኩዋሲህ አፒያህ በራስ መተማመን እንደሚያሳድግ የአገሪቱ ሚዲያዎች አውስተዋል፡፡ ጋና ከኢትዮጵያ በኋላ ለዓለም ዋንጫ የምታደርገውን ዝግጅት ቀጥላለች ሰሞኑን ከሜኬሲኮ ጋር ተገናኝታ 1ለ0 የተሸነፈች ሲሆን በቀጣይ ደግሞ ከአሜሪካ ጋር የምትጫወት ይሆናል፡፡  የአፍሪካ ዋንጫ ለ4 ጊዜያት ያሸነፈችው ጋና በሰኔ ወር የፊፋ ወርሃዊ የዓለም እግር ኳስ ደረጃ በ678 ነጥብ 49ኛ ላይ የምትገኝ ሲሆን የተጨዋቾች ስብስቧ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 55.17  ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡ በሌላ በኩል ለዋልያዎቹ የአፍሪካ ዋንጫ የማለፍ ተስፋ በጋና ባጋጠመው የመጀመርያ ጨዋታ ከባድ ሽንፈት የሚያበረታታ አልሆነም፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን 10 ጊዜ በመሳተፍ አንድ ጊዜ ሻምፒዮን ሆናለች፡፡ በሰኔ ወር የፊፋ ወርሃዊ የዓለም እግር ኳስ ደረጃ በ265 ነጥብ 125ኛ ላይ የምትገኘ ሲሆን፤ የተጨዋቾች ስብስቧ በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ 723ሺ ዩሮ ነው፡፡
ከመጀመርያው ዙር ጨዋታ በኋላ ምድብ 6ን ጋና በ3 ነጥብ እና በ5 የግብ ክፍያ ስትመራው ሴራሊዮን በ3 ነጥብ እና በ1 የግብ ክፍያ 2ኛ ሆናለች፡፡ ኬንያ በ1 የግብ እዳ ሶስተኛ ደረጃን ስትይዝ ኢትዮጵያ በ5 የግብ እዳ የመጨረሻውን ደረጃ ይዛለች፡፡ የምድብ ማጣርያው 2ኛ ዙር ጨዋታዎች ከ8 ወራት በኋላ ሲቀጥሉ ኢትዮጵያ ከሴራሊዮን እንዲሁም ኬንያ ከጋና ይገናኛሉ፡፡ ከ14 ወራት በኋላ  ደግሞ የ3ኛና የ4ኛ ዙር ጨዋታዎች በሁለት ሳምንት የደርሶ መልስ ትንቅንቅ  ሲቀጥሉ በመጀመርያ ጋና ከሴራሊዮን እንዲሁም ኢትዮጵያ ከኬንያ እንዲሁም ከ1 ሳምንት በኋላ በመልስ ጨዋታ ሴራሊዮን ከጋና እንዲሁም ኬንያ ከሴራሊዮን ይጫወታሉ፡፡ ከ15 ወራት በኋላ በ5ኛ ዙር ጨዋታ ኢትዮጵያ ከጋና እንዲሁም ኬንያ ከሴራሊዮን እንዲሁም በ6ኛ ዙር ጨዋታ ሴራሊዮን ከኢትዮጵያ ጋና ከኬንያ ይገናኛሉ፡፡
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከሁለት ሳምንት በፊት አክራ ከተማ ላይ ከገጠመው የ5ለ0 ሽንፈት በኋላ ብዙ የትችት ሃሳቦች ተንፀባርቀዋል፡፡ ዋልያዎች በቂ ዝግጅት እያደረጉ አይደለም፡፡ በፌደሬሽኑ በኩል ተገቢውን ትኩረት ያጡም ይመስላል፡፡  ቀደምት ዋልያዎችም በየክለቦቻቸው ስኬታማ ቢሆኑም በብሄራዊ ቡድኑ ያላቸው ሚና መዳከሙ ብዙዎችን ያስገረመ ነው፡፡   ከደቡብ አፍሪካ መልስ ፕሪሚዬር ሊጉን በኮከብ ግብ አግቢነት ሪከርድ አስመዝግቦ ያሸነፈው ጌታነህ ከበደ፤ በግብፅ ሊግ ሁለት ክለቦች በግብ አዳኝነት እና በኮከብ ተጨዋችነት የተሳካላቸው ኡመድ እና ሽመልስ፤ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ኮከብ ግብ አግቢነት የሚገኘው የቅዱስ ጊዮርጊሱ ሳላዲን እንዲሁም ሰሞኑን የሩስያውን ክለብ ለመቀላቀል የበቃው ጋቶች ፓኖም የዋልያዎቹ አባላት ከመሆናቸው ጋር በተያያዘ ለወደፊቱ ብዙ ተግባራ መሰራት ይኖርባቸዋል፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ስኬታማ እንዲሆን የፋይናንስ አቅሙ ማሟላት፤ ለተጨዋቾች የማበረታቻ ክፍያዎች ማዘጋጀት፤  የወዳጅነት ጨዋታ እና በቂ የዝግጅት መስጠት ተገቢ ነው፡፡

      የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን እንዲሁም የኢትዮጵያ ቡና ክለብ ተጨዋችና አምበል ሆኖ ያገለገለው ጋቶች ፓኖም የራሽያውን ታዋቂ ክለብ አንዚ ማካችካላ ተቀላቀለ፡፡ የ23 ዓመቱ ጋቶች ይህን በኢትዮጵያ እግር ኳስ አዲስ ምዕራፍ የሚከፍት ዝውውር ያሳካው ከኢትዮጵያ ቡና ጋር የነበረው የቅጥር ውል ካበቃ በኋላ ነው፡፡  ባለፈው ሰሞን ለሙከራ ወደ ራሽያ ተጉዞ የነበረው ተጨዋቹ በሙከራ ጨዋታ ላይ ጎል ካገባ በኋላ የክለቡን ሃላፊዎች እና አሰልጣኞች ስለማረካቸው፤ የዝውውሩን ሂደት ስኬታማ አድርጎታል በማለት የተጨዋቹ ወኪል  ሆኖ የሰራው ትውልደ ጀርመናዊው ዴቪድ በሻህ በሰጠው መግለጫ አስታውቋል፡፡ ጋቶች በራሽያ ፕሪሚያራ ሊግ ተፎካካሪ ከሆኑ ክለቦች ዋንኛ ተጠቃሽ  የሆነውን አንዚ ማካችካላ በመቀላቀል መጫወት የሚጀምረው ከ2017 -18 እኤአ የውድድር ዘመን ጀምሮ ሲሆን የውል ስምምነቱ ለ3 ዓመታት የሚቆይ   ነው፡፡  
በተከላካይ አማካይ እና በመሃል አማካይ መስመሮች የሚጫወተው ጋቶች  ከአውሮፓ ታላላቅ ሊጎች ቀጥሎ በሚመደበው ራሽያ ፕሪሚዬራ ሊግ በመጫወት የመጀመርያው ኢትዮጵያዊ ሲሆን ይህም በኢትዮጵያ እግር ኳስ አዲስ የስኬት ደረጃ ሆኖ ሊጠቀስ ይችላል።    አንዚ ማካችካላ  ለ2017-18 ዘመን ለሚያደርገው ዝግጅት ጋቶች ፓኖምን ጨምሮ    ሌሎች 10 ተጨዋቾችን ያስፈረመ ሲሆን ከታዋቂዎቹ ሲኤስኬ እና ዳይናሞ ሞስኮ ያዛወራቸው ይገኙበታል፡፡ በተጨዋቾ ስብስቡ ከ6 የተለያዩ  አገራት ፕሮፌሽናሎች ጨምሮ 29 ተጨዋቾችን ያስመዘገበው የሩሲያው ክለብ  የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 18.4 ሚሊዮን ዮሮ እንደሆነ ታውቋል፡፡
ከጋቶች ፓኖም የራሽያ ዝውውር በኋላ የተሰሙ አንዳንድ መረጃዎች በአንዚ ማካች ካላ በሳምንት 5ሺ ዩሮ እንደሚከፈለው የገለፁ ሲሆን  በዝውውር ገበያው የዋጋ ተመኑ ከግማሽ ሚሊዮን ዩሮ በላይ ሊሆን እንደሚችል ተገምቷል፡፡ ይህም በኢትዮጵያ እግር ኳስ ውዱ ተጨዋች ሊያደርገው ይችላል፡፡
ከጋቶች ፓኖም ሻገር የሌሎቹ ዋልያዎች የዝውውር ገበያ ግምትና ወቅታዊ ውጤታማነት
ሽመልስ በቀለ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 400ሺ ዩሮ ነው፡፡ የግብፅ ክለብ ፔትሮጄት የሚገኘውና በቀኝ እና ግራ አማካይ መስመሮች የሚጫወተው ሽመልስ  ባለፈው 1 ዓመት በግብፅ ሊግ እና ካፕ ላይ በ22 ጨዋታዎች 5 ጎሎችን አስመዝገቧል፡፡
የ28 ዓመቱ ሳላዲን ሰኢድ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 300ሺ ዩሮ ነው፡፡ ዘንድሮ በቅዱስ ጊዮርጊስ ማልያ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ከቅድማጣርያው አንስቶ በ7 ጨዋታዎች በመሰለፍ 4 ጎሎች አስመዝግቧል፡፡
ኡመድ ኡክሪ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 200ሺ ዩሮ ነው፡፡ በ2014 15 የውድድር ዘመን በአልኢትሃድ፤ በ2015 በኤንፒፒአይ እየተጫወተ ከፍተኛ ልምድ ያካበተው ኡመድ ከ2016 በጀምሮ በግብፁ ኤል ኤንታግ ኤልሃረቢ እየተጫወተ ሲሆን በግብፅ ሊግ እና ካፕ ላይ በ29 ጨዋታዎች 11 ጎሎችን አስመዝገቧል፡፡
ጌታነህ ከበደ አሁን በሚጫወትበት የደደቢት እግር ኳስ ክለብ በወቅቱ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመኑ 150ሺ ዩሮ ነው፡፡ ከዓመት በደቡብ አፍሪካ ሁለት ክለቦች ቢድቬስት ዊትስ እና በፕሪቶርያ ሲጫወት በ56 ጨዋታዎች በመሰለፍ 13 ጎሎች ያስመዘገበው ጌታነህ ዘንድሮ በኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግ ኮከብ ግብ አግቢነት ጨርሷል፡፡

 - አሁን የምናመርተው እስራኤል 70 ኣመት ከተጠበበችበት ምርት ይበልጣል
                 - እኛ ፋብሪካ ውስጥ ፈተና ወድቆ መምጣት ነውር ነው
                 - ፋብሪካው ትንሽ ገቢ ሲያገኝ ለሰራተኞችም ጭማሪ ይደረጋል

          በ1978 ዓ.ም ነው አራት ህፃናት ልጆቻቸውንና ባለቤታቸውን ይዘው ወደ እስራኤል የተሻገሩት፡፡ የሄዱበት ምክንያት ደግሞ ነፃ የትምህርት እድል በማግኘታቸው ነበር፡፡ ደሴ ከተማ ውስጥ ተወልደው ያደጉት አቶ አሰፋ አስናቀ መንገሻ፤ በወጣትነት እድሜያቸው በአየር ኃይል፣ በግብርና ሚኒስቴርና በተለያዩ መስሪያ ቤቶች የሰሩ ሲሆን ከመጀመሪያዎቹ የህብረት ስራ ማህበራት አደራጆች አንደኛው እንደነበሩ ይናገራሉ፡፡ በጠቅላላው ወደ 10 ዓመታት ያህል ከሰሩ በኋላ በ1977 ዓ.ም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ገብተው በአካውንቲንግ የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን ያገኙት አቶ አሰፋ፤ በዓመቱ ነፃ የትምህርት ዕድል አግኝተው፣ አራት ህፃናት ልጆቻቸውንና ባለቤታቸውን ይዘው ወደ እስራኤል መጓዛቸውን ይገልፃሉ፡፡ በእስራኤልም “ሰርቲፋይድ አካውንቲንግ” ካጠኑ በኋላ በአካውንታንትነት ሙያ ተቀጥረው ሲሰሩ ቆይተዋል፡፡ ከቅጥር ወጥተው የራሳቸውን ድርጅት በመክፈት ለተለያዩ ኩባንያዎች የአካውንቲንግ አገልግሎት ሲሰጡ እንደነበር የሚናገሩት አቶ አሰፋ፤ ከ22 ዓመታት በኋላ ወደ አገራቸው ተመልሰው በሰንዳፋ ኢንዱስትሪ ዞን “አፍሮ አምክሰላር ኢነርጂ ቴክ” የተሰኘ በፀሐይ ሀይል የሚሰሩ የውሃ ጋኖችንና የፀሐይ ሀይል የሚሰበስቡ ፓኔሎችን የሚያመርት ፋብሪካ አቋቁመው በመስራት ላይ ይገኛሉ፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከአቶ አሰፋ ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡

    ከኢትዮጵያ ከወጡ ከ22 ዓመታት በኋላ እንዴት ነው ወደ አገርዎ የተመለሱት?
ከኢትዮጵያ ከወጣሁ በኋላ በአንድ ወቅት አንድ ሁለት ጊዜ መጥቼ ነበር፡፡ ብቅ ብዬ ነው የተመለስኩት። በመጣሁበት ወቅት ገና ለውጥ መጀመሩ ነበር፤ የመጣሁትም አባቴ አርፎ ለለቅሶ ነበር፡፡ ተመልሼ ሄድኩኝ፡፡ ገና ልማት አልተጀመረም ነበር፡፡ ወደ እስራኤል ተመልሼ ከሄድኩ በኋላ ለ22 ዓመታት ወደ ኢትዮጵያ አልመጣሁም፡፡ ከዚህ ሁሉ ዓመት በኋላ ወደ ኢትዮጵያ እንድመጣ ያበረታታችኝ ባለቤቴ ናት፡፡
እንዴት?
ባለቤቴ በእስራኤል አገር የትምህርት ዲቪዥን ኃላፊ ናት፡፡ በአንድ ወቅት ከእስራኤል አገር ለስራ ትልልቅ እንግዶችን ይዛ፣ ወደ ኢትዮጵያ ከመጣች በኋላ የተወለድንበትን አካባቢ ጎብኝታ፣ የተለያዩ አካባቢዎችን አይታ፣ ያለውን ለውጥ እንድመለከት ነገረችኝ፡፡ ከዚያም አብረን መጥተን፣ ሁሉንም ተዘዋውረን አየን፡፡ እንደገና ተመልሼ ብቻዬን መጣሁና ሁሉን ነገር በሚገባ ተመለከትኩኝ፡፡ እኔ ኢትዮጵያ በነበርኩበት ጊዜ ከአዲስ አበባ እስከ ገጠር ስለሰራሁ፣ ያን ጊዜ የነበረውን የመሰረተ ልማት ችግሮች አውቅ ነበር፡፡ አሁን እነዚያ ነገሮች ሙሉ በሙሉ ባይሆንም በጥሩ ሁኔታ ተለውጠው አየሁኝ፡፡ ይህን ስመለከት እኔስ እዚህ መጥቼ ለአገሬ ምን ላድርግ፣ የሚለውን ጥያቄ ራሴን ጠየኩኝ፡፡ ይህን ያሰብኩት እ.ኤ.አ በ2011 ነበር፡፡ ከዚያም እስራኤል የምሰራውን ስራ ትቼ ወደ ኢንዱስትሪ ለመግባት ወሰንኩ፡፡ የተለያዩ ቢዝነሶችንም ማጥናት ጀመርኩኝ፡፡ እውነት ለመናገር እኔ ለአገሬ ቀናተኛ ሰው ነኝ፡፡ እዚያ የለሙ ነገሮችን ሳይ፣ የሆነ ነገር ተለውጦ ስመለከት፣ ምን ነበር አገሬ ላይ ቢሆን እላለሁ፡፡ ከዚህም የተነሳ ነው ሳጠና የሶላር ኢነርጂው ጉዳይ የመጣልኝ፡፡
በዘርፉ ለመሰማራት የመረጡበት ምክንያት ምንድን ነው?
የኖርኩባት አገር እስራኤል ከተመሰረተችበት ጊዜ ጀምሮ በፀሐይ ኃይል በኩል ከፍተኛ ተጠቃሚ ናት፡፡ በተለይ በፀሐይ ኀይል የምታለማው የመስኖ ስራ ከፍተኛ ነው፡፡ እኔም ሶስት አራት ዘርፎችን ግምት ውስጥ ካስገባሁ በኋላ በተለይ ዓለም በአሁኑ ሰዓት በኃይል እጥረት በተወጠረበትና የኢትዮጵያ መንግስት በታዳሽ ሀይልና በአረንጓዴ ልማት ላይ ትኩረት ባደረገበት በዚህ ዘመን፣ የፀሐይ ሀይልን በመጠቀም የውጭ ምንዛሬ ከማዳንና የኤሌክትሪክ ሀይል ብክነትን ከመታደግ እንዲሁም የስራ እድል ከመፍጠርም አኳያ አቻ የማይገኝለት ስራ ነው በሚል ነው “አፍሮ አምክሶላር ኢነርጂቴክ” የተሰኘውን ፋብሪካ በሰንዳፋ ኢንዱስትሪ ዞን ውስጥ የከፈትኩት፡፡ በነገራችን ላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ስለ ፀሐይ ሀይል ካለው ግንዛቤ፣ ዘርፉ ለአገራችን አዲስ ከመሆኑ አኳያ ብዙ ፈተናዎች እንደሚገጥሙኝ ባውቅም ኃላፊነቱን ወስጄ ነው ያቋቋምኩት፡፡
ፋብሪካውን በማቋቋም ሂደት የገጠምዎት ተግዳሮቶች አሉ?
ፈተናው የጀመረው ሀሳቡን ለዘመድ ወዳጅ ማማከር በጀመርኩበት ጊዜ ነው፡፡ በተለይ እኔም ባለቤቴም በውጭ ስንኖር፣ በስራችን ባህሪ ምክንያት ከህዝቡ ጋር ብዙ ትውውቅና ቅርርብ ነበረን፡፡ ብዙ ፈረንጅ ጓደኞቻችን ሀሳቡን ስንነግራቸው፣ እንደ እብደት ነበር ያዩት፡፡ አፍሪካ ውስጥ ያውም ሶስተኛ ዓለም ላይ እንዴት ይህን ታስባለህ በማለት፣ እኔ እንዳልበረታታ ብዙ ግፊቶች ነበሩ፡፡ አንዱ ፈተና ይሄ ነበር፡፡ ያንን ፈተና ማለፍ ቻልኩኝ፡፡ ኢትዮጵያ በህዝቧ ጥረትና ብዛት፣ ባላት የተፈጥሮ ሀብትና ባለሙያዎች፣ ወደፊት ተስፋ ያላት አገር መሆኗን ስለማውቅ፣ ዛሬ ባይሳካ ነገ ይሳካል በሚል፣ የጓደኞቼን ምክርና ተግሳፅ ወደ ጎን ትቼ፣ በሀሳቤ ገፋሁ፡፡ በኋላ ደግሞ ኬኒያ፣ ታንዛኒያና ሩዋንዳ ያሉ ዲፕሎማቶች ሀሳቤን ሲሰሙ፣ ከእኛ ጋር በአጋርነት ለምን አትሰራም የሚል አማላይ ሀሳብ አቀረቡና ትንሽ ግራ መጋባት ውስጥ ገብቼ ነበር፡፡ ይህንንም ከራሴ ጋር መክሬ ተውኩት፡፡ በምንም ሚዛን የአገሬን ያህል አይሆኑም፡፡
ይህን ካለፉ በኋላ የፋብሪካው ግንባታ ምን ይመስል ነበር?
እኔ በሀሳቤ ከፀናሁ በኋላ በእስራኤል የኢትዮጵያ አምባሳደር የነበሩት አቶ ህላዌ ዮሴፍ በጉዳዩ ገብተውበት፣ የአቶ ታደሰ ኃይሌ ድጋፍ ተጨምሮበት፣ በሰንዳፋ ኢንዱስትሪ ዞን በመረጥነው ቦታ ላይ 3 ሺህ ካሬ ሜትር ወሰድኩኝ፡፡ ቦታውን ለማግኘት ብዙ አልተቸገርኩም። ከዚያ በኋላ በራሴ ገንዘብ ግንባታ ጀመርኩና ብድር ጥየቃ ወደ ባንክ ሄድኩኝ፣ ይሄ ቴክኖሎጂ በብዙ ዘርፍ ለአገሪቱ ጠቃሚ ነውና ብድር ስጡኝ ስል፣ ገንዘብ የለንም አሉኝ፡፡ ቴክኖሎጂው ጠቃሚ ስለመሆኑ ሚኒስትሮቹና ባለሙያዎች እየመሰከሩ፣ እኔም ትልቅ ፍላጎትና ተነሳሽነት እንዳለኝ ለማሳየት ከሚደግፉኝ ሰዎች ጋር ሆኜ፣ በራሴ ገንዘብ እየገነባሁ፣ ፈፅሞ ብድሩን ለማግኘት አልቻልኩም።
ከባንክ ምን ያህል ነበር የጠየቁት ብድር?
በወቅቱ ፋብሪካውን ለማቋቋም ከ16 ሚ. ብር በላይ ያስፈልግ ነበር፡፡ እኔም የጠየኩት 16 ሚ. ብር ነው። ነገር ግን ይህን ብድር ለማግኘት ከ2 ዓመት በላይ ተጉላልቻለሁ፡፡ ሆኖም ግንባታው ቀጥሎ ነበር፡፡ በአንድ በኩል እነዚህ ብድር ፈቃጆች የፕሮጀክቱ ጥቅም ላይ ግንዛቤ ስላልነበራቸው አልፈርድባቸውም፡፡ ሆኖም ጉዳዩን ከልብ አዳምጠው መረዳት ይችሉ ነበር፤ ግን ትኩረት አልሰጡትም፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ትልልቆቹ ኃላፊዎች ጉዳዩን ጠንቅቀው ያውቁት ነበር፡፡ በኋላ ከስር ያሉት ሰዎች፤ “ይሄ ለኢትዮጵያ አስፈላጊ ፕሮጀክት አይደለም” የሚል ውሳኔ ላይ ደረሱ፡፡
ከዚያስ?
ያንን ውሳኔ ሲወስኑ የኢነርጂ ሚኒስትር ወደነበሩት ወደ አቶ ዓለማየሁ ተገኑ ሄድኩና የተከለከልኩበትን ደብዳቤ ሰጠኋቸው፡፡ በወቅቱ ተበሳጩ፡፡ ስልክ ደውለው ይሄን ቴክኖሎጂ እንዴት ትገፋላችሁ ብለው ተናገሩ። ከዚያ እንደገና ጉዳዩ ይታይ ተባለና፣ በባለስልጣኖቹ ድጋፍ ከሞላ ጎደል ብደሩ ተፈቀደ፡፡
ከሞላ ጎደል ሲሉ ከጠየቁት ብድር ምን ያህሉን አገኙ?
አልወሰኑም እንዳይባሉ ከጠየኩት 16 ሚ. ብር 11 ሚ. ብር ፈቀዱ፡፡ ትንሽ ቆዩና ፕሮጀክቱን በተግባር ሲመለከቱ እንደገና 1.3 ሚ. ፈቀዱና ብድሩ በጠቅላላ 12.3 ሚሊዮን ብር ሆነ፤ ያንን ለማግኘት ብዙ ጊዜ ፈጀ፤ ያንን አልፈን ምርት ተጀመረ፡፡
መቼ ነው ማምረት የጀመራችሁት?
ባለፈው ዓመት ነሀሴ ላይ ማምረት ጀመርን። አሁን በመኖሪያ ቤቶች፣ በሆቴሎች፣ በሻወር ቤቶች በአዲስ አበባም ሆነ በሌሎች ምርታችን በተፈለገበት ቦታ እየሄድን እንገጥማለን፡፡ በብዙ ኮንቴይነር ከሌላ ቦታ የሚገባውንና ለዚያ የሚወጣውን የውጭ ምንዛሬ ለማዳን ችለናል፡፡ ያለማጋነን ምርታችን እስራኤል አገር ካሉ ምርቶች በጥራት ይበልጣል፤ ይሄንን እርግጠኛ ሆኜ መናገር እችላለሁ፡፡
በፀሐይ ሃይል ውሃ ለማሞቅ ምን ያህል ጊዜ ይፈጃል? ምን ያህል የኤሌክትሪክ ኃይልስ ይቆጥባል?
ይሄ በጣም ጥሩና አስፈላጊ ጥያቄ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ከውጭ አገር የሚገቡት በፀሐይ ኃይል ውሃ የሚያሞቁ በርሜሎች አብዛኞቹ 200 ሊትር ናቸው፡፡ እኛ ግን አማራጮችን አስቀምጠናል፡፡ ለምሳሌ ባልና ሚስት ከሁለት ልጆቻቸው ጋር የሚኖሩ ከሆነ፣ 200 ሊትር ውሃ ምን ያደርግላቸዋል? 80 ሊትር በቂ ነው፡፡ ወጥ ቤትም ውስጥ ሙቅ ውሃ መጠቀም እፈልጋለሁ ካልሽ፣ 150 ሊትር ከበቂ በላይ ነው፤ የግድ 200 ሊትር ስላለ ብቻ ሰውን ያንን ግጠም ብሎ ማስገደድ አግባብ አይደለም። አንዱ ይሄ ነው፡፡ ሁለተኛው በፀሐይ ኃይል ለመሞቅ የሚወስደው ጊዜ እንደየወቅቱና አካባቢው ቢለያይም፣ በአማካይ ግን የሁለት ሰዓት የፀሐይ ሙቀት 200 ሊትር ውሃ በደንብ ያሞቃል፡፡ በ80 እና በ150 ሊትር ግን በበርሜል ውስጥ የፈላ ውሃ ታገኛለሽ፡፡ እኛ አገር በጣም ክረምት በሚባለው በሐምሌና ነሐሴ ወር እንኳን ዝናብ ከመዝነቡ ከአንድና ሁለት ሰዓት በፊት ፀሐይ ይወጣል፤ ያኔ ሙቅ ውሃ አለ፤ ፀሐይ ጭራሹኑ በማይኖር ጊዜ ማሞቂያችን በኤሌክትሪክ ሲስተምም ስለሚሰራ፣ ያኔ ግድ ከሆነ ኤሌክትሪክ መጠቀም ይቻላል፡፡ የኛ የፀሐይ ኃይል ሲስተም ከፍተኛ ኢንሱሌሽን ያለው ነው፤ አንዴ ከሞቀ ለረጅም ጊዜ ሙቀት አፍኖ የመያዝ አቅም ስላለው ቶሎ አለመቀዝቀዙ ከሌላው ይለየናል፡፡
ምን ያህል የኤሌክትሪክ ሀይል ይቆጥባል የሚለውን አልመለሱልኝም …
በጣም ጥሩ! በእያንዳንዱ 200 ሊትር የፀሐይ ኃይል ውሃ የሚያሞቅ በርሜል 7 ኪሎ ዋት ኢነርጂ እንቆጥባለን። በ150 ሊትርም ቢሆን 7 ኪሎ ዋት ትቆጥቢያለሽ፡፡ ይሄን ሀይል መንግስት ለሌላ በርካታ ስራ ያውለዋል፡፡ እኛ ይህንን የምንለው በኪሎ ካሎሪ ነው፤ ያንን ወደ ኢነርጂ ስንለውጠው የምንቆጥበውን ኃይል እናውቀዋለን፡፡ ይሄ የእስራኤል ሳይንቲስቶች ቀመርና የ70 ዓመት ልምድ ነው፡፡ ይህን ደግሞ ከፍ አድርገን እንመልከተው፡፡ ለምሳሌ እኛ 1 ሺህ ማሞቂያዎችን ብንገጥም፣ ከ7 እስከ 10 ሜጋ ዋት ኃይል በቀን ለመንግስት ይቆጠብለታል፡፡ ይሄ ማለት የቆቃ ሀይል ማለት ነው፡፡ ቆቃ እስከ 90 ሜጋ ዋት ነው ያመርታል የሚባለው፡፡ ቀላል አይደለም፡፡ በነገራችን ላይ ክቡር አለማየሁ ተገኑ ፋብሪካውን መጥተው ጎብኝተው፤ “መቼ ነው ማስፋፊያ የምትጀምረው?” ብለው ጠይቀውኛል። ከስራቸውም ጋር ቀጥተኛ ግንኙነት ስላለው ከፍተኛ ድጋፍ አድርገውልናል፡፡ እርሳቸው ባይደግፉኝ ህልሜ እውን አይሆንም ነበር፡፡ “ይህንን ስራ አስፋፍተህ የአዲስ አበባን የኤሌክትሪክ ውሃ ማሞቂያ ጠራርገህ አውጣልኝ” ነው ያሉት፡፡ ይሄ የሚያመለክተው መንግስት ምን ያህል የኃይል እጥረት እንዳለበትና ተጨማሪ አጋዥ ቴክኖሎጂ እንደሚያስፈልገው ነው፡፡ ከጥቂት አመታት በፊት ለአዲስ አበባ ከተማ ብቻ በቀን ወደ 400 ሜጋ ዋት ሀይል ያስፈልግ ነበር፡፡ በአሁኑ ጊዜ ወደ 700 ሜጋ ዋት አድጓል። እኛ እድሉንና ድጋፉን ካገኘን ይህንን ሀይል መቆጠብ እንችላለን፡፡ ይህን የምናደርገው የህዝቡን ግንዛቤ አሳድገን፣ ፋብሪካችን ተስፋፍቶና ገበያውን ሰብረን ስንገባ ነው፡፡ በዚህ ረገድ አሁንም ከመንግስት ብዙ ድጋፍ እንፈልጋለን፡፡
በአገራችን በተለይም በአዲስ አበባና ዙሪያዋ እየተስፋፋ ከመጣው የፋብሪካ ብዛትና የኃይል አቅርቦት አለመመጣጠን አንፃር ከውሃ ማሞቂያ ይልቅ የሚያስፈልገው መብራት ይመስለኛል፡፡ መንግስትም ይህን ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ከውጭ በፀሐይ ሀይል የሚሰሩ መብራቶችን ቢያስገባም፣ አብዛኞቹ ለብልሽት እንደተዳረጉ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ እርስዎ ከመብራት ይልቅ እንዴት ለውሃ ማሞቂያዎች ቅድሚያ ሰጡ? ወደፊትስ በፀሐይ ኃይል የሚሰሩ መብራቶችን ለህብረተሰቡ ለማቅረብ ያሰቡት ነገር የለም?
ከጥያቄሽ በመነሳት ሁለት ነገሮችን ልመልስ … ሰው በሀይል እጥረት መብራት ይቆራረጥበታል፤ አዎ እውነት ነው፡፡ ግን በተወሰነ የሰዓት ገደብ መብራት ያገኛል። መታጠቢያን ስትመለከቺ፣ አብዛኛው ሰው በሙቅ ውሃ የመታጠብ እድሉ ዝቅተኛ ነው፡፡ ይሄን ከኢኮኖሚ አለማደግ ጋር እናያይዘዋለን፡፡ ለምሳሌ በኤሌክትሪክ ኃይል እንጀራ ለመጋገር፣ ውሃ አሙቆ ለመታጠብ፣ የኢኮኖሚ አቅማቸው የማይፈቅድ ብዙ ናቸው፡፡ ይሄ ግን አንዴ ማሞቂያ ፓኔሉን ካስገቡ በነፃ ነው የሚጠቀሙት። ቆጣሪ የለውም፤ ክፍያ የለውም፤ ተፈጥሮን ብቻ ነው የሚጠቀሙት፡፡ ሁለተኛው ነገር ወደ ገጠሩ ወጣ ብለን እንዳየነው ከሆነ፤ አሁን አሁን ሰዎች ሻወር ቤት እየገነቡ፣ በፀሐይ ሀይል ውሃ የሚያሞቅ በርሜልና ፓኔል እየገጠምንላቸው፣ ለህብረተሰቡ በተመጣጣኝ ዋጋ አገልግሎት እየሰጡና እነሱም እየተጠቀሙ ነው፡፡ በሀይል ቁጠባም በኩል ካየሽው፣ ከመብራት (ከአምፖል ይልቅ) የውሃ ማሞቂያው ብዙ ሀይል ስለሚፈጅ፣ ለውሃ ማሞቂያው ቅድሚያ ሰጥተናል፡፡ የውጭ ምንዛሬንም ማስቀረት ችለናል፡፡
ይሁን እንጂ በፀሐይ ሀይል ብርሃን የሚሰጥ መብራት የመስራትም እቅድ አለን ግን አሁንም ከፍተኛ ገንዘብ፣ ትልቅ ፋብሪካ ይፈልጋል፡፡ እኛ መንግስት ድጋፍ ካደረገልን፣ በዚህም በኩል ዓለም አቀፍ ጥራቱን የጠበቀ ምርት የማምረት እውቀቱም ብቃቱም አለን፡፡ ከተማውንም ሆነ ገጠሩን የመብራት ተጠቃሚ ማድረግ እንችላለን፡፡ መንግስት ፋይናንሱን ከሰጠን ከ6-8 ወር ባለ ጊዜ ውስጥ ጥራቱን የጠበቀ ምርት ማምረት እንችላለን። በሰራተኞቻችን እውቀትና የስልጠና አቀባበልም እንተማመናለን፡፡
በፀሐይ ኃይል የሚሰራ መብራት ለማምረት ብድር ጠይቃችሁ ነበር?
ሁልጊዜ እንጠይቃለን፤ ከውጭ አይምጣ፤ ጥራት ያለው የፀሐይ መሰብሰቢያና ለመብራት የሚውል እቃ ላምርት ብዬ ብዙ ጊዜ ብጠይቅም ፋይናንስ የለም ነው መልሳቸው፡፡ በቃ በዚህኛው ተገድቤ እየሰራሁ ነው፡፡
እስኪ በፋብሪካችሁ ስለሚሰሩ ሰራተኞቻችሁ ይንገሩኝ፡፡ የትምህርት ደረጃቸው እንዴት ነው? የሠራተኛ አያያዛችሁ ምን ይመስላል?
በነገራችን ላይ እኔ መንግስትን ከማደንቅበት አንዱ የቴክኒክና ሙያ ት/ቤቶችን አስፋፍቶ፣ ወጣቶች በተለያዩ ደረጃዎች ሰልጥነው፣ ራሳቸውን እንዲችሉ ማድረጉ ነው፡፡ እርግጥ ነው ቀደም ሲልም እንደነ ፖሊቴክኒክ፣ ተግባረ ዕድ ያሉ የስልጠና ተቋማት ነበሩ፡፡ ነገር ግን እነዚህ በከፍተኛ ደረጃ ነው ስልጠና የሚሰጡት። አሁን መንግስት ያስፋፋቸው የቴክኒክና ሙያ ት/ቤቶች በርካታ ዕድል ላላገኙ ወጣቶች እድል ሰጥተዋል፡፡ እነዚህ እድል ያላገኙ የነበሩት ደግሞ በጣም ጥሩ ጥሩ ጭንቅላት ያላቸው ልጆች ናቸው፡፡ የእኛን ፋብሪካ ቀጥ አድርገው የያዙትም ከትልልቅ ዩኒቨርሲቲዎች በኤሌክትሪካል ወይም በሜካኒካል ኢንጂነሪንግ የተመረቁ እንዳይመስሉሽ፤ ከቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ የመጡ ብቁ ወጣቶች ናቸው፡፡ ከፍተኛ ስልጠና እንዲያገኙ ከውጭ አገር ኤክስፐርቶችን ለሳምንት ለ10 ቀን እናመጣለን። እነሱ በ3 ቀን ስልጠና ሁሉን አውቀው ያጠናቅቁና በቃ ፈረንጁን ወደ አገሩ መልሰው ይላሉ፡፡ አሁን እየሰሩ ያሉት በትልቅ ብቃት ነው፡፡ አያያዝንና እንክብካቤን በተመለከተ፣ እኔ ከምናገር እነሱ ቢጠየቁ የተሻለ ይሆን ነበር፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው ውጤታማ ስራ ለመስራት ከፈለገ፣ ሰራተኞቹን መንከባከብ፣ እንደ ቤተሰብ ቀርቦ ችግራቸውን መረዳት፣ የአቅም ግንባታ ስልጠና መስጠት፣ እውቀታቸው እንዲያድግ፣ ጥሩ የስራ ከባቢ እንዲኖራቸው ማድረግ የግድ ይመስለኛል፡፡ እኛ ይህን እናደርጋለን፡፡ እኛ ጋ እየሰሩ የትምህርት ደረጃቸውን እያሳደጉ የሚገኙ አሉ። የፈተናና የጥናት ሰዓታቸው ይከበራል፡፡ እኛ ፋብሪካ ውስጥ ፈተና ወድቆ መምጣት ነውር ነው፡፡ በጣም ታማኝና ቅን ሰራተኞች ናቸው፡፡ ነገ በስራቸው ሌሎችን አሰልጥነው ተክተው፤ እነሱ የራሳቸውን ስራ እንዲሰሩ የማድረግ እቅድ አለኝ፡፡ በሌላው ፋብሪካ እንደምታዘበው፣ ለስልጠናና ለአቅም ግንባታ ሰራተኞቻቸው ላይ ብዙ ብር አፍስሰው ሲያበቁ ጥለዋቸው ይሄዳሉ፡፡ እኔን እስካሁን ጥሎኝ የሄደ ሰራተኛ የለም፤ ቢሄዱም ከኔ የተሻለ እንክብካቤና ደሞዝ አግኝተው ከሆነ ቅር ሊለኝ አይገባም፡፡ እስካሁን ያለው ይሄን ይመስላል፡፡ እኛ አሁን ከሌቭል አንድ የወሰድናቸው ነበሩ፡፡ እዚህ እየሰሩ ሌቭል ሁለትና ሶስትን ተምረው፣ ሲኦሲ አልፈው፣ ወደ ከፍተኛ ትምህርት ለመግባት የሚያስቡ አሉ፡፡ ክፍያን በተመለከተ ተመጣጣኝ ክፍያ እንከፍላለን፡፡ ፋብሪካው ትንሽ ገቢ ሲያገኝ ለእነሱም ጭማሪ ይደረጋል፡፡ ከደሞዛቸው ውጭም ሲስተም ለመትከል ስንሄድ የሚያገኙት ገንዘብ አለ፤ ለተከሉበት ማለት ነው፡፡ እኔም ሲስተም እንዲገጥሙ ስወስዳቸው የውሎ አበል እከፍላለሁ፡፡ ሁሉም የተሻለ ክፍያ እንደምከፍላቸው ያውቃል፡፡ አንድ ስራ ከያዙና ካልጨረሱ ምሳ ለመብላት እንኳን ፈቃደኛ አይደሉም፡፡ እንዲህ ዓይነት ታማኝና ጠንካራ ሰራተኞች አለመንከባከብ ውድቀት ነው፡፡ እነዚህ ልጆች ከቴክኒክና ሙያ ነው የመጡት፤ ግን ሰውን መፍጠር ይቻላል፡፡
የውሃ ማሞቂያዎችን በምን ያህል ዋጋ ነው የምትሸጡት? ሲስተሙን ለመግጠም ተጨማሪ ክፍያ ትጠይቃላችሁ?
ዋጋን በተመለከተ 80 ሊትሩን የውሃ ማሞቂያ ቫትን ጨምሮ በ13, ሺህ 500 ብር፣ 150 ሊትር ቫትን ጨምሮ በ17 ሺህ ብር፣ 200 ሊትሩን ደግሞ 22 ሺህ 500 ብር እንሸጣለን፡፡ ሄደን በምንገጥምበት ጊዜ ለባለሙያዎች 700 ብር ገዢው ይከፍላል፤ ያ 700 ብር ወደ እኛ አይመጣም፤ ወደ ገጣሚዎቹ ነው የሚሄደው፡፡
ፋብሪካው በአሁኑ ወቅት የማምረት አቅሙ ምን ያህል ነው? የፈላጊውስ መጠን?
 ፋብሪካው አሁን ባለበት ሁኔታ በወር 3 ሺህ በርሜሎችንና የፀሐይ ኃይል የሚሰበስቡ ፓኔሎችን የማምረት አቅም አለው፡፡ ፈላጊው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ነው፡፡ ሆቴሎች፣ ግለሰቦች፣ ባለ ሻወር ቤቶችች፣ ጤና ጣቢያዎች እየጠየቁን፣ በክልልም በአዲስ አበባም ምርታችንን እያቀረብን እንገኛለን፡፡ አሁን ህዝቡ ግንዛቤ እያገኘ ነው፡፡ ወደፊት ገበያውን ሰብረን እንገባለን፤ ያኔ አሁን ከምናቀርብበት ዋጋ በጣም ባነሰ ለማቅረብ ያስችለናል፡፡ ምክንያቱም ብዙ ባመረትንና በሸጥን ቁጥር ከውጭ የሚመጡ መሳሪያዎችን እዚህ ማምረት እንጀምራለን፡፡ በተጨማሪም ከውጭ በተዘዋዋሪ የምናስገባቸውን የፋብሪካ ግብአቶች ቀጥታ ከአምራቾች የምንረካከብበትን ሁኔታ የመፍጠር አቅም ይኖረናል፣ ይሄ ይሄ ወጪያችንን ስለሚቀንስልን አሁን ከምናቀርብበት ዋጋ በጣም በመቀነስ፣ ዝቅተኛ ገቢ ያላቸውም የእድሉ ተጠቃሚ እንዲሆኑ እናደርጋለን ማለት ነው፡፡
ምን ያህል ሰራተኞች አሏችሁ?
በአሁኑ ወቅት ከ19 እስከ 22 የሚደርሱ ሰራተኞች አሉን፡፡ ስንጀምር የፋብሪካው መነሻ ካፒታል 16 ሚ. ብር ነበር፤ ሲሆን አሁን ከ30 ሚ. ብር በላይ ካፒታል ያንቀሳቅሳል፡፡
የወደፊት ዕቅድዎ ምንድን ነው?
በመጀመሪያ ደረጃ ህብረተሰቡ ግንዛቤ ኖሮት፣ መንግስትም ዋነኛ አጋዥ ኃይል መሆኑን በመገንዘብ ይበልጥ አግዞን፣ ሁሉም ህብረተሰብ ተቋማት፣ ዩኒቨርሲቲዎች፣ ሆስፒታሎች የቴክኖሎጂው ተጠቃሚ እንዲሆኑ ማድረግ ነው አላማዬ፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ህዝቡም አውቆት የመንግስት ድጋፍ ተጠናክሮ ቀጥሎ፣ ካደግን በአጎራባች አገሮች ያለውን ገበያ መያዝና የውጭ ምንዛሬ ማስገኘት፣ ኢትዮጵያ በሶላር ኢነርጂ ከሌላው ዓለም የተሻለች መሆኗን ማሳየት ሌላውና ትልቁ አላማችን ነው፡፡ ምክንያቱም 13 ወር ሙሉ የፀሐይ ፀጋ ያላት በተፈጥሮ የታደለች አገር ናት፡፡ ሌላው ለውጭ ገበያ ደረጃውን የጠበቀ የዘርፉን ምርቶች ማቅረብና ሁሉንም መስራት እንደምንችል ለሌላው ዓለም ማሳየትም የአፍሮአምክ ሌላው ራዕይ ነው ይህን ማድረግ ይቻላል፡፡ አሁንም የምናመርታቸው ምርቶች እስራኤል 70 ዓመት ከተጠበበችበት ምርት ይበልጣል፡፤
ከዚያ ቀጥሎ ዋናው ዓላማችን የኤሌክትሪክ መፍጠሪያውን መሳሪያ አገራችን ላይ አምርተን ማሳየት ነው፡፡ ይሄ እንደውም በቅርቡ ቢሆን ትልቅ ምኞት አለን፡፡ ለዚህ ዋና እንቅፋት የሆነብን ፋይናንስ እንጂ እውቀትና ብቃት አለን፡፡ ቢሮክራሲው እስከለቀቀንና ፋይናንስ እስካገኘን ድረስ መስራት እንችላለን፡፡ ፈረንጅ ላይ ጥገኛ መሆን አያስፈልገንም፡፡ በቃ በአገራችን ልጆች እውቀት እንመን፤ መልዕክቴ ነው፡፡ በተረፈ እዚህ ለመድረስ ብዙ ፈተናዎች ቢገጥሙኝም ያንን እንዳልፍ የረዱኝን ቤተሰቦቼን፣ የመንግስት ኃላፊዎችንና ጓደኞቼን እንዲሁም ዓላማዬን ራዕዬን ተረድታችሁ፣ ፍላጎቴንና ስራዬን ለህብረተሰቡ እንድናገር እድል የሰጣችሁኝን የጋዜጣችሁን ዝግጅት ክፍል ከልቤ አመሰግናለሁ፡፡

የስራ አመራር መፅሐፍትን በመፃፍ የሚታወቁት በአቶ እሸቱ እንደሻው የተፃፈውና መልካም ባህሎችና ልምዶች ላይ የተመሰረተ የሰለጠነ ማህበራዊ ስርዓት መገንባትን ዓላማው አድርጎ የተፃፈው “የሰለጠነ ማህበራዊ ሰው” መፅሐፍ የዛሬ ሳምንት ከቀኑ 9፡00 ሰዓት ጀምሮ በራስ ሆቴል አዳራሽ ይመረቃል፡፡ በምረቃ ስነ-ስርዓቱ ላይ የተለያዩ ኪነ ጥበባዊ ስራዎችና በመፅሐፉ ላይ ዳሰሳ ይቀርባልም ተብሏል። መፅሐፉ የሳይንስና ቴክኖሎጂ እመርታን፣ ስኬትን፣ደስታን፣ ምሳሌያዊ አነጋገሮችን፣ ፍቅርና ቤተሰብን የሚዳስሱ ሀሳቦችንና ተያያዥ ጉዳዮችን ይዟል፡፡ 112 ገፆች ያሉት ይኸው መፅሃፍ በ80 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

  እ.ኤ.አ በ1972 ጥቅምት ወር መግቢያ ላይ የኡራጓይ የአየር ሀይል የመጓጓዣ አውሮፕላን የአንድ የራግቢ ክለብ ተጫዋቾችን እና ደጋፊዎቹን አሳፍሮ ከዋናው ከተማ ከሞንቲ ቪዲዮ ወደ ቺሊ ዋና ከተማ ሳንቲያጎ በመብረር ላይ እያለ በከፍተኛነቱ ከሚታወቀው አንድስ ተራራ ላይ ወድቆ የራግቢ ተጫዋቾቹና ደጋፊዎቻቸው ለ71 ቀናት በበረዶ ላይ ያሳለፉትን ስቃይ ከስቃዩ ተረፉትንና ህይወታቸው ያለፈውን ተጓዦች ጉዳይ የሚያወሳው የተራራው ምርኮኞች መፅሐፍ በድጋሚ ታትሞ ለንባብ በቃ፡፡ በደራሲ ፒየር ፖል ሪድ የተፃፈውና በሀዲስ እንግዳ አይቼህ የተተረጎመው ይህ መፅሐፍ እውነተኛ ታሪኩ አጃኢብ ያሰኘና አ ደጋውም የ ዓለም አቀፍ የ ዜና ሽፋን ያገኘ ሲሆን ታሪኩ ወደ መፅሐፍና ወደ ፊልም ተቀይሮ ብዙ አንባቢና ተመልካች ማግኘቱ የሚታወስ ነው፡፡ መፅሐፉ በ321 ገፅ ተፅፎ በ150 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

  እናት የማስታወቂያ ድርጅት ከጀርመን የባህል ማዕከል (ጎተ) ጋር በመተባበር ነገ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቤተ መፃህፍትና ቤተ መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ “አለመኖር” በተሰኘው የዶ/ር ዳዊት ወንድም አገኝ መፅሐፍ ላይ ውይይት ያካሂዳል፡፡ በእለቱ ለውይይት የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት የስነ-ፅሁፍ ባለሙያው አቶ በአካል ንጉሴ እንደሆኑ የገለፀው እናት የማስታወቂያ ድርጅት ፍላጎት ያለው በውይይቱ ላይ እንዲሳተፍ ጥሪ አቅርቧል፡፡

  እስካሁን ለምን ዝም እንዳልኩኝ የምትረዱ ይመስለኛል፡፡ ድንጋጤና ሐዘን በጣም ጎድተውኛል፤ በትክክል ሁሉ ማሰብ አልቻልኩም ነበር፡፡ አሴ ቢሆን ስንት ፅፎ ነበር፡፡
በመጀመሪያ ለአባቴ የደረሰችለት ዳላስ ቴክሳስ የምትኖረው ወ/ሮ አብነት ከነቤተሰቧ፤ ተመላልሳ በመጠየቅ ከአጠገቡ የተገኘች መልካም ሴት ናት፡፡ መቼም ቢሆን አልረሳሽም፤ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡ መላው ቤተሰብ እንዲያውቅ አብነትንም ወደ አሴ እንድትሄድ ያደረጉ የአክስታችን የእትዬ ሽታ ልጆች ትዕግስትና ኤልሳ ምክሩ በጣም ኮርቼባችኋለሁ፣ የእትዬ ሽታ ምትክ ናችሁ።
አሴ አገሩ እንዲገባ ትልቁን ሚና የተጫወቱት በዳላስ ቴክሳስ የኢትዮጵያ ኮሚኒቴ፤ ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻ ገንዘብ አሰባስበው የሚያስፈልገውን ሁሉ በማድረግ፣ ከሆስፒታል ጀምሮ እስከ አሸኛኘቱ ድረስ ለፍተው ብዙ ጥረት በማድረጋቸው እንዲሁም በአሜሪካ በተለያዩ ስቴቶች እንዲሁም በተለያዩ ውጭ አገራት ያላችሁ የአሴ ወዳጆች፣ ጓደኞች ሁሉ ያደረጋችሁትን መረባረብ ታሪክ አይረሳውም፡፡
በዳላስ ደብረ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራል አስተዳዳሪና የቅዱስ ተቋም ዳይሬክተር፣ ቀሲስ አንዱዓለም ዳግማዊ፣ እግዚአብሔር ብድራቱን ይክፈላችሁ እላለሁ፡፡
በድጋሚ በዳላስ ቴክሳስ የኢትዮጵያ ኮሙኒቲና በሌላውም ስቴት ያላችሁ፣ በመላው አለም የምትገኙ ኢትዮጵያውያን ሁሉ እሱ እንደወጣ እንዳይቀር ስላደረጋችሁ ደግሜ ደግሜ አመሰግናለሁኝ፡፡
ኢትዮጵያ ሲገባ ደግሞ ከመግባቱ ዜና ጀምሮ እስከ የቀብር ሥነ ሥርዓቱ ድረስ ህዝብ እንዲያውቀው በማድረግ ትልቁን ሚና የተጫወተው ሸገር 102.1 ሬዲዮ በጣም አመሰግናለሁ፡፡ እኛ ለአንድም ሰው ደውለን አልተናገርንም፤ ሁሉንም ያሰባሰባችሁት እናንተ ናችሁ። አባቴን እንዳከበራችሁት እግዚአብሔር ያክብርልኝ። በተለይ አቶ ደምሰውንና ሌሎችንም የሸገር አዘጋጆች በሙሉ፣ ወ/ሮ መዓዛንም ላመሰግን እወዳለሁ፡፡
ኢትዮጵያ ሲገባ ከቦሌ ጀምሮ አቀባበል በማድረግና በሁለተኛው ቀንም የቀብር ስነ ስርአቱን በደማቅ ሁኔታ ያስከበሩትን የኢትዮጵያ ሕዝብ ታላቅ ምስጋና አቀርባለሁ፡፡›
በሌላ በኩል በአርባ ምንጭና በጨንቻ የቀብር ሥነ ሥርአቱ ይፈፀማል ብለው በጣም ሰፊ ዝግጅትና ድካም ሲያደርጉ የቆዩትን የአርባ ምንጭ ህዝብና የክልሉን መንግስት ይቅርታ እጠይቃለሁኝ፡፡ ያም ሳያንሳችሁ እዚህ ድረስ በመምጣት የቀብር ሥነ ሥርአቱ በባህሉ መሰረት፣ እዚህ ካለው ህዝብ ጋር በደማቅ ሁኔታ ስለአከበራችሁ አመሰግናለሁ፡፡
ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች የምትልኩልን የሐዘን መግለጫ ደርሶናል፡፡ ለዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች፣ ለምሁራን፣ ለባለሥልጣናት፣ ለአምባሳደሮች፣ ለሚኒስትሮች፣ ለውጭም ሆነ ለአገር ውስጥ ጋዜጠኞች፣ ለአሴ የቅርብ ጓደኞችና ወዳጆች ከአጠገባችን ላልተለያችሁን ሁሉ እናመሰግናለን፡፡
የአባቴ የቅርብ ጓደኛና (ወንድም) አቶ ፍቅረ ማርያም ይፍሩ፤ አባቴ አገሩ ሲገባ ከአቀባበል ጀምሮ የህይወት ታሪኩን ባመረ ሁኔታ ፅፎ ያቀረበው የቤተክርስቲያኑ ፕሮግራም እንዲያ እስከ መጨረሻው ድረስ እንደ ሰርግ አምሮ ደምቆ እንዲደረግ የለፋ በመሆኑ እግዚአብሔር እድሜና ጤና ይስጠው እላለሁ፡፡
የአክስቴ ባለቤት አቶ ባልቻ ሙሊሣ፤ የአክስት ባለቤት ሊባል አይቻልም፤ አይገባውም፡፡ ለኛ አባታችን መሰብሰቢያችን ነው፡፡ አሁንም የአሴን ማረፍ ከሰማ ቀን ጀምሮ ቤተሰቡን ከየአለበት እንዲሰባሰብ በማድረግ፣ ደከመኝ ሳይል ያንን ሁሉ ቀን ቤተሰባችንን በመሰብሰብ የቀብሩ ሥነ ስርዓት በጥሩ ሁኔታ ተፈፅሞ፣ እንግዶች በስርአት እንዲሸኙ በማድረግ ትልቅ ነገር ነው ያደረገው፡፡ እግዚአብሔር እድሜና፣ ጤና ይሰጥልን፡፡
ለቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አስተዳዳሪ፣ ለካቴድራሉ ቀሳውስት፣ ካህናት ለአገልጋዮች በአጠቃላይ፣ ለቀሲስ ፀጋዬ በክብር ስለሸኛችሁት በልዑል እግዚያብሄር ስም አመሰግናለሁ፡፡
እንደ ሃሳቡና ፍላጎቱ እንደ ዶርዜ ወንድሞቼ፣ እንደ ጋሞ ዘመዶቹ በዋፈራና በሆታ ሸኙኝ ባለው መሠረት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳትሉ በድምቀት ከጥዋት ጀምራችሁ እስከ ቀብር ሥነሥርአቱ ድረስ ላሳመራችሁለት የልቡን ስለፈፀማችሁ፣ ለአቶ ሞላ ዘገየ እንደ ቤተሰብ መሀላችን ገብተህ የኢትዮጵያዊነትህን፣ የወንድምነትህን፣ የጓደኝነትህን ከሌሎች ከውጭም ከአገር ውስጥም ካሉ ጋር በመተባበር እስከመጨረሻው ከአጠገባችን ባለመለየት የሰማነውን የህይወት ታሪክ ባማረ ሁኔታ አሰማሀን፡፡
ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ አዘጋጆች (የአሴ ወዳጆች)፣ ለነብይ መኮንንና ለአለማየሁ አንበሴ እንዲሁም ለሌሎቹ ጋዜጠኞች በሙሉ ከመጀመሪያ ካረፈበት ግዜ አንስታችሁ ሰፊ ሽፋን ነው የሰጣችሁት፤ አስቀድሜ እንዲያውም በጣም ፈርቼ ማዘኔን ነግሬአችሁ ነበር፡፡ ብቻችንን ነን ብዬም ነበር፤ ኋላ ሁሉም ደረሰልን፡፡ አመሰግናለሁ፡፡
ለነባዳን የሚዲያ ማማከር ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር (ለዳኒና ለነብይ) ለደራሲ እንዳለ ጌታና ለወሰን ሰገድ ገ/ኪዳን፣ ለዘነበ ወላ … በአሜሪካን አገር ለሚኖሩ አባቴን እንደ አባት የሚጠብቁና የሚቆረቆሩለት ዳንኤል ካሣሁንና ዶክተር ግርማ አውግቸው ደመቀ እንዲሁም ለካሣሁን ሰቦቃ … ምስጋናዬ ይድረሳችሁ፡፡
ለቤት አከራዮቼ (እንደ አባትና እናት) ለሚሆኑልኝ፣ በሐዘኔ በአጠገቤ ላልተለዩት ለአቶ ሲሳይ ወልተጂና ለወ/ሮ መለሰች ሁሪሳ ከነልጆቻቸው እንዲሁም ለጎረቤቶችና ለጓደኞቼ ለመላው ቤተሰብ ለሻምበል ሃ/ገብርኤል ጫቦና ቤተሰቡ፣ ለወ/ሮ ግንብነሽ ጫቦ ከነልጆቿ፣ ለወ/ሮ ቃልኪዳን መሸሻ፣  ለወ/ሮ ተቀባሽ አንጣልና ብርሃን አንጣል ከነልጆቻቸው፣ ለአቶ ሳምሶን አሰፋ ከነቤተሰቡ፣ ለአቶ አለማየሁ አሰፋ፣ ለአቶ ዋሴ አዛዥ ከነቤቴሰቡ ለአቶ የማነ ከነቤተሰቡ፣ ለአቶ ባንጃው ወዜ ከነቤተሰቡ፣ ለአቶ ፈለቀ በፀሎት ከነቤተሰቡ፣
ለውድ ባለቤቴ ለአቶ በላይ ይመርና ለልጆቼ እንዲሁም በስም ላልጠቀስኳቸው ብዙ ወዳጆቻችን … አመሰግናለሁ፡፡
ለድሬድዋ ነዋሪዎችና ለከተማዋ አስተዳደር ለወንድሜ የኤፍሬም አሰፋ ጫቦ ጓደኞችና ጎረቤቶች ሁሉንም… አመሰግናለሁ፡፡
ከኢትዮጵያ ውጭ ላሉ የሬዲዮና ቴሌቪዥን አዘጋጆችና ጋዜጠኞች በሙሉ …
በኢትዮጵያም ሆነ፣ በውጭ አገር ለምትኖሩ ሁሉ … ላደረጋችሁልን፣ ለአባቴ ለከፈላችሁት መስዋዕትነት ሁሉ እግዚአብሔር ይክፈላችሁ፤ አመሰግናለሁኝ፡፡
በመጨረሻ ለፍቶ እንዲያው እንዳይቀር በአገር ውስጥ አንድ የስሙ መጠሪያ እንዲደረግለትና “ቁጥር ሁለት የትዝታ ፈለግ” አባቴ ፅፎ ጨርሶ ነውና ያረፈው፤ ያንንም እቀጥላለሁኝ፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ከአጠገቤ እንደማይለይ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
እመቤት አሰፋ ጫቦና ቤተሰቦቿ

Sunday, 02 July 2017 00:00

‘የተሳሳተ ጥሪ’

  እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ከጥቂት ሳምንታት በፊት ነው፡፡ አንድ ወዳጄ አንድ ቀን ከምሽቱ አምስት ሰዓት ገደማ ስልክ ይደወልለታል። በዛ ሰዓት ይደውልልኛል ብሎ የሚያስበው ሰው ስላልነበር፣ የልብ ምቱ ትንሽ ፈጠን ይላል፡፡
“ሄሎ፣ ማን ልበል!” ይላል፡፡
በምላሹ “ሄሎ፣ እከሌ ነኝ፣” የለ፣ “ናፍቀኸኝ ነው” የለ፣ “ድንገት ትዝ ብለኸኝ ነው፣” የለ… “ፖለቲከኛው አለቃህ አሁንም ነክሶህ እንደያዘህ ነው ወይ!” ...ብቻ የሆነች ሴት ድምጽ በአንድ ሴከንድ ስድሳ ያህል ቃላት ታርከፈክፍበታለች፣ የስድብ ቃላት። በእሷ ዐይን ኤልሱን በጣም ጭምት፣ እንደ ኤሊ እየተንቀረፈፈች የምትናገር ነች፡፡ ቂ…ቂ...ቂ… ኧረ እሱ ላይ የደረሰው ነገር አያስቅም፡፡ ሊያስበው የሚችለውንና፣ የማይችለውን የስድብ አይነት ላይ በላይ ትዘረግፍበታለች፡፡ ስድቦቹ አይደለም በዚህ ዘመን በድሮው የ‘ሬድ ላይት’ ሰፈሮች እንኳን የተረሱ ናቸው፡፡ ከእሱ ጋር ቤተሰቦቹ አልቀሩ፣ ጓደኞቹ አልቀሩ፣ ሁሉም ‘የድርሻቸው’ ተሰጣቸው። ወላ ነጠላ ሰረዝ፣ ወላ አራት ነጥብ የሌለው አጥንት ሰባሪ ዘለፋ ታወርድበታለች፡፡ ቢቸግረው ስልኩን ይጠረቅመዋል፡፡ እንደገና ስትደውል አያነሳም፡፡ ደጋግማ  ስትደውል ለክፉም ለደጉም ብሎ ያነሳዋል።
“አንተ ማን አባክ ሆንክና ነው የምትዘጋብኝ!…” ብላ የአዲስ አበባን ቀለበት መንገድ ሦስት እጥፍ የሚረዝም የስድብ መአት ትደረድርለታለች። “ምን አለች በለኝ…” ብላ ታላላቅ ባለስልጣኖች እንደምታውቅ፡ ልቡ እስኪጠፋ እንደምታስጠበጥበው ፎከራ… “አንተን ልክ ካላስገባሁ ከምላሴ ጸጉር!” ምናምን ብላ ትዘጋበታለች፡፡
እኔ የምለው መጀመሪያ ስም አይቀድምም እንዴ!  “አንተን ማን ልበል፣” ምናምን አይነት ማረጋገጫ!
በማግስቱ በጊዜ ይደወላል ያው ቁጥር፡፡ አያነሳውም። ደጋግሞ ከተደወለ በኋላ “እባክህ ስልኩን አንሳልኝ፣” የሚል የጽሁፍ መልእክት ይደርሰዋል፡፡ ቀጥሎ ሲደወል ይነሳል፡ እያለቀሰች ይቅርታ ትጠይቀዋለች፡፡ ለካስ የገዛ ጓደኛዋን ይዞ የፈነገላት ‘ቦይፍሬንዷ’ መስሏት ነው፡፡ አሀ… ‘ቦይፍሬንድ’ስ ቢሆን ይሄን ያህል መሰደብ አለበት እንዴ! ማንኛውም ጨረታ ላይ እኮ “ድርጅቱ የተሻለ መንገድ ካገኘ ጨረታውን ማስተላለፍም ሆነ መሰረዝ ይችላል…” ምናምን የሚባል ነገር አለው (ሴትዮዋ ከሰማችን ሁለተኛው ዙር ለእኛ ነው፡፡)
በተለይ ደግሞ ከመሸ በኋላና በሌሊት የሚደውሉ የተሳሳቱ ጥሪዎች የምር አስቸጋሪ ናቸው፡፡
ይቺን ስሙኝማ፡፡ የቴሌፎን ኩባንያው ፕሬዝደንት ሌሊት እንቅልፉን ይለጥጣል፡  ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት ገደማ ስልኩ ሲጮህ ይነቃል፡፡
“ሄሎ!”
“ሄሎ፣ የቴሌፎን ኩባንያው ፕሬዝደንት ነህ?”
“አዎ ነኝ፣  ምን ልርዳዎ?”
“እስቲ ከሌሊቱ ስምንት ሰዓት በተሳሳተ ጥሪ ከሚጣፍጥ እንቅልፍህ መቀስቀስ ምን እንደሚመስል አሁን ንገረኝ!” አለውና አረፈው፡፡
እናማ ‘የተሳሳተ ጥሪ’ ነገር አስቸጋሪ ነው፡፡
እናማ…ይሄ ‘የተሳሳተ ጥሪ’ ነገር የምር አስቸጋሪ ነው፡፡ የምር አሁን፣ አሁን የማትጠየቁት የሰው አይነት፣ የመሥሪያ ቤት አይነት የለም፡፡ አሁን እኔ ምኔ ‘እንትን ጋራዥ’ን ይመስላል! ቂ…ቂ…ቂ…  እናማ… ጥሪው ‘ከመሳሳቱ’ ሌላ የደዋዮቹ ባህሪይ ከአገር ሊያሰወጣን ምንም አልቀረው…  ከአገር የሚያስወጡ ነገሮች ያልበዙብን ይመስል!
ከአገር የመውጣት ነገር ካነሳን፣ ከዚህ በፊት አንስተናት ልትሆን የምትችል ነገር ላውራችሁማ። ‘በዛኛው ዘመን’ የሆነ ነው፡፡ ውጪ ተምሮ የመጣ ሰው ነው፡ ለምርምር ወደ ምዕራብ ኢትዮጵያ ይላካል። ታዲያላችሁ… “ይህ ሰውዬ ድብቅ የፖለቲካ ዓላማ ሳይኖረው አይቀርም ተብሎ  እያንዳንዱ እንቅስቃሴው በወታደር ይጠበቃል፡፡ ታዲያ ጧት፣ ጧት እየተነሳ ይሮጣል፣ ወታደሮችም ይከተሉታል። ይሀ ነገር ለተወሰነ ጊዜ ይቀጥልና ከወታደሮቹ ይላመድና በራሱ እየሮጠ መመለስ ይጀምራል። ታዲያ አንድ ቀን በወጣበት ይቀራል፡፡ በሳምንቱ ገደማ… “ሩጫ ስለፈቀዳችሁልኝ አመሰግናለሁ፣” የሚል የስልክ ጥሪ ይደርሳል...ከኖርዌይ። (ሩጫ በሸታና እድሜን ማባረሪያ ብቻ ሳይሆን ‘መብረሪያ’ ሊሆን ይችላል ለማለት ያህል ነው።)
“ሄሎ!”
“ሄሎ፣ ማን ልበል?”
“ሄለንን አቅርብልኝ፡፡”  ጥያቄ ሳይሆን ትእዛዝ፡፡
“ጌታዬ ተሳስተዋል፡ ሄለን የሚባል ሰው የለም፡፡”
“አታቀርብልኝም፣ ማለት ነው?”
“ጌታዬ እንደዛ የሚባል ሰው የለም አልኩዎት እኮ!”
“በአንተ ቤት ማታለልህ ነው! ደግሞ ንገራት፣ እናትሽ ሆድ ብትገቢ አታመልጪኝም በላት፡፡ ይሄ የምትኩራሪበትን መልክሽን የህጻናት ማስፈራሪያ ባላደርገው እኔ አይደለሁም ብሏል በላት!”  ጥርቅም!
ሰውየው ይደውልና…
“ይሄ ቁጥር ስንት ነው?” ይላል፡፡ በወዲያኛው ጫፍ ያለው ምን ብሎ ቢመልስለት ጥሩ ነው… “አንተ ንገረኝ እንጂ፣ አንተ አይደለህ እንዴ የደወልከው?” አሪፍ መልስ አይደል!
እኔ እኮ ይሄ ሞባይል የሚሉት ነገር…ፎካሪው መብዛቱ! “ተሳስተዋል፣” “ሌላ ቁጥር ነው የደወሉት፣” እያላችሁት ያለ ጋሻና ጦር ቀረርቶውን ይለቅባችኋል። ሄለን የለችም ማለት፣ “ሄለን የለችም” ማለት አይደለም እንዴ!
ሀሳብ አለን…የተሳሳተ ቁጥር በደወሉ ጊዜ ምን ማለት እንደሚገባዎ የሁለት ወር ልዩ የክረምት ስልጠና ምናምን ይዘጋጅልን፡፡ አሀ..እነሱ በተጣሉት፣ እነሱ በተፈነጋገሉት፣ እነሱ በተካካዱት…እኛ ስድቡን የመሸከም ውል ተዋውለናል እንዴ!
“ሄሎ!”
“ሄሎ!”
“እስቲ ባንጃውን አቅርብልኝ…” ቁጣ፡፡
“ይቅርታ፣ ተሳስተዋል፡፡”
“ስማ፣ ሄደህ የምታሾፍበት ላይ አሹፍ፡፡ አሁን ባንጃውን ታቀርብልኛለህ፣ አታቀርብልኝም!”
ባንጃው ምንም ያድርግ ምን ጦሱ ወደ እናንተ ይመጣል፡፡ (ስሙ ግን ብዙ ነገር ማድረግ የሚችል ያስመስለዋል፣ ቂ…ቂ..ቂ…)
“ጌታዬ ምናልባት ሲደውሉ ቁጥር ተሳስተው ይሆናል፡፡”
ጆሯችሁ ላይ ጥርቅም!
ለነገሩ ዘንድሮ የባህሪይ ነገር፣ የስነ ምግባር ነገር ግራ እየገባን “ሰውረነ ከመአቱ…” አይነት የሚያስብል ሆኗል። ስልክ ደግሞ ሳይታዩ እንደልብ ለመሆን ስለሚያመች ይኸው እንግዲህ የተነጠቀውም፣ የተፈነገለውም፣ የተጭበረበረውም…እኛ ላይ ንዴቱን ይወጣል፡፡
ለመሳሳቱ እናንተ ምክንያት የሆናችሁ ይመስላል። ከተናደደ ቴሌ ጆሮ ላይ አይጠረቅመውም እንዴ!
እንግዲህ ባንጃው ማን ይሁን፣ ምን ይሁን የሚያውቅ ይወቀው፡፡
ይቺን ስሙኝማ…ሰውየው በኦፕሬተር በኩል ይደውላል፡፡  
“ሄሎ!”
“ሄሎ፣ እንዴት ይዞሀል?”
“ደህና ነኝ፡፡ ስማ ትንሽ ብር ስለቸገረኝ መቶ ብር ያህል በባንክ ላክልኝ፡፡”
ድምጹ ይለወጣል፡፡ “ስልኩ ይንኮሻኮሻል…የምትለው አይሰማኝም፡፡”
“መቶ ብር በባንክ ላክልኝ ነው ያልኩህ…”
“ምን አይነት ስልክ ነው… የምትለው ምንም አይሰማኝም!”
ይሄኔ ኦፕሬተራ ጣልቃ ትገባና “እኔ የሚለው ይሰማኛል፣” ትላለች፡፡ ይሄኔ አጅሬው ምን ቢል ጥሩ ነው…
“እንግዲያው መቶ ብሩን አንቺ ላኪለት፡፡”
ደህና ሰንብቱልኝማ!