Administrator

Administrator

  የቻይና የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪ መስክ መሃንዲሶች ለመጀመሪያ ጊዜ በባለሶስት አውታር ማተሚያ ማሽን (3D printer) አትመው ያወጧትን ቀላል መኪና ሃይናን በተባለችው የአገሪቱ ግዛት ውስጥ ለእይታ ማብቃታቸውን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
3.6 ሜትር ቁመትና 1.63 ሜትር ስፋት ያላትን ይህቺን መኪና፣ በቀላል ወጪ የሚገዙ ቁሳቁሶችን በግብዓትነት በመጠቀም በማተሚያ ማሽኑ አማካይነት ሰርቶ ለማጠናቀቅ፣ አምስት ቀናትን ብቻ እንደፈጀ የጠቆመው ዘገባው፣ ክብደቷም አነስተኛ እንደሆነ ገልጧል፡፡
የመኪናዋ ዋና ዲዛይነር የሆኑት ቼን ሚንጊያኦ እንዳሉት፤ ባለ ሁለት መቀመጫዋ መኪና ክብደቷ አነስተኛ ቢሆንም ጥንካሬን የተላበሰች ናት ብለዋል፡፡ ክብደቷ አነስተኛ መሆኑ ደግሞ ሃይል ለመቆጠብ ያስችላታል ሲሉም ተናግረዋል፡፡ ከኮምፒውተር ጋር በተያያዘ ባለሶስት አውታር ማተሚያ አማካይነት ቁሳቁሶችን ማተም የሚያስችለውን የዘመኑ ቴክኖሎጂ በመጠቀም በቻይና ታሪክ የመጀመሪያዋ የሆነችው ይህቺ መኪና፣ ቻርጅ ከሚደረግ ባትሪ በምታገኘው ሃይል የምትንቀሳቀስ ሲሆን በሰዓት እስከ 40 ኪሎ ሜትር ርቀት የመጓዝ አቅም አላት፡፡

Monday, 06 April 2015 09:06

የየአገሩ አባባል

ለጅል መድሃኒቱ ሞት ብቻ ነው፡፡
በፀሐይ እረስ፣ በዝናብ አንብብ፡፡
ያልተጠየከውን ምክር አትለግስ፡፡
አንዳንዴ መድኀኒቱ ከበሽታው ይከፋል፡፡
የጫማ ሰሪ ልጅ ሁልጊዜ በእግሩ ይሄዳል፡፡
ስጦታ የሚቀበል ነፃነቱን ይሸጣል፡፡
መንሾካሾክ ባለበት ሁሉ ውሸት አለ፡፡
ገንዘብ የሌለው ሰው ገበያ ውስጥ ጥድፍ ጥድፍ ይላል፡፡
አንዴ የሰረቀ ሁልጊዜ ሌባ ነው፡፡
ሆድ ሲሞላ ልብ ደስተኛ ይሆናል፡፡
ቁራ ካረባህ ዓይንህን ይጓጉጡታል፡፡
ማልዶ የተነሳ ያልደፈረሰ ውሃ ይጠጣል፡፡
ጥርጣሬ የዕውቀት ቁልፍ ነው፡፡
ፅጌረዳውን የፈለገ እሾሁን ማክበር አለበት፡፡
ዓይነስውር በራሰ በራ ይስቃል፡፡
እባብ ለመያዝ የጠላትህን እጅ ተጠቀም፡፡
ነፋስ ያመጣውን ነፋስ ይወስደዋል፡፡
ልብ ውስጥ ያለውን ምላስ ያወጣዋል፡፡
በወጣት ትከሻ ላይ አሮጌ ጭንቅላት መትከል አትችልም፡፡
ሰነፍ በግ ፀጉሩ የከበደው ይመስለዋል፡፡

   አሜሪካ ለግብጽ ስትሰጥ የቆየችውንና ለሁለት አመታት ያህል አቋርጣው የነበረውን ወታደራዊ ድጋፍ እንደገና ሙሉ ለሙሉ መስጠት ልትጀምር እንደሆነ ማስታወቋን ዋሽንግተን ፖስት ዘገበ፡፡ የኦባማ አስተዳደር ለግብጽ ሲሰጠው የቆየውንና ከ2013 ጥቅምት ወር ወዲህ አቋርጦት የነበረውን 1.3 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት አመታዊ የወታደራዊ መሳሪያዎች ድጋፍ እንደገና ለመጀመር ውሳኔ ላይ መድረሱን ባለፈው ክሰኞ አስታውቋል፡፡የግብጹ ፕሬዚዳንት ሞሃመድ ሙርሲ ከስልጣን መውረዳቸውን ተከትሎ፣ አገሪቱ እስከምትረጋጋና ዲሞክራሲያዊ ማሻሻያዎችን ተግባራዊ ለማድረግ የሚያስችል ተጨባጭ ለውጥ እስኪታይ ድረስ፣ አሜሪካ ለግብጽ የምትሰጠውን ወታደራዊ ድጋፍ አቋርጣ መቆየቷን ዘገባው አስታውሷል፡፡ የአሜሪካ መንግስት ወታደራዊ ድጋፉን እንደገና ለመስጠት መወሰኑ፣ ግብጽን ከፍተኛ ዋጋ የሚያወጡ አሜሪካ ሰራሽ የወታደራዊ መሳሪያዎች ባለቤት ያደርጋታል ያለው ዘገባው፣ ላለፉት ሁለት አመታት በአሜሪካ እጅ የቆዩ 12 ኤፍ-16 ተዋጊ ጀቶችን፣ 20 ቦይንግ ሃርፖን ሚሳየሎችን፣125 አሜሪካ ሰራሽ አብራምስ ኤምዋንኤዋን ታንኮችንና ሌሎች መሳሪያዎችን ማግኘት እንደሚያስችላት የአሜሪካ ብሄራዊ የደህንነት ካውንስል ቃል አቀባይ በርናዴት ሜሃን መናገራቸውን ጠቁሟል፡፡  አሜሪካ ወታደራዊ ድጋፉን እንደገና ለመቀጠል የወሰነችው፣ የራሷን የብሄራዊ ደህንነት ፍላጎት መሰረት በማድረግ ነው ያሉት ቃል አቀባይዋ፣ ለግብጽ የምትሰጠውን ወታደራዊ ድጋፍ በተለይ ሽብርተኝነትን ለመዋጋት፤ የድንበርና የባህር ደህንነቶችን ለማስጠበቅና አይሲሲ የተባለው ታጣቂ ቡድን በሲናይ አካባቢ የሚያደርገውን እንቅስቃሴ ለመግታት በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ላይ እንዲውሉ በሚያስችል መልኩ ማሻሻሏንም አስታውቀዋል፡፡ ኦባማ ክግብጹ ፕሬዚዳንት አል ሲሲ ጋር ባደረጉት የስልክ ውይይት፣ 1.3 ቢሊዮን ዶላር የሚገመተውን ወታደራዊ ድጋፍ በዘላቂነት ለማስቀጠል ለአሜሪካ ምክር ቤት ጥያቄ እንደሚያቀርቡ ቃል ገብተዋል፡፡ ግብጽ ከ2018 ጀምሮ የጦር መሳሪያዎችን በብድር መግዛቷን ማቆም እንደሚገባት አሳስበዋቸዋል፡፡አልጀዚራ በበኩሉ፤ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት አሜሪካ ለግብጽ ሙሉ ወታደራዊ ድጋፍ ለመስጠት መወሰኗ እንደሚያሳስባቸው መግለጻቸውን ጠቅሶ፣ ሂውማን ራይትስ ፈርስት የተባለው ተቋም ዳይሬክተር ኔል ሂክስ “አሜሪካ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ለሚታዩባት ግብጽ ድጋፏን ለመቀጠል መወሰኗ ለሰብዓዊ መብቶች መከበር ቅድሚያ አትሰጥም የሚል አደገኛ መልዕክት ሊያስተላልፍ ይችላል” ማለታቸውን ዘግቧል፡፡አሜሪካ ባለፈው አመት ተመሳሳይ ወር ለግብጽ የምትሰጠውን ድጋፍ በከፊል እንደምትጀምር ማስታወቋን ያስታወሰው ዘገባው፣ ግብጽ ከአሜሪካ ከፍተኛ ወታደራዊ ድጋፍ በማግኘት ከእስራኤል ቀጥላ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝም ጠቁሟል፡፡

Monday, 06 April 2015 08:58

የፍቅር ጥግ

ፍቅር ልዩ ቃል ነው፡፡ የምጠቀምበት ከልቤ ሲሆን ብቻ ነው፡፡ ቃሉን ደጋግማችሁ ስትሉት ይረክሳል፡፡
ሬይ ቻርልስ
ድንገት በጭጋጋማው የለንደን ከተማ ውስጥ አየሁሽ፡፡ ፀሐይዋ ሁሉን ስፍራ አድምቃው ነበር፡፡
ጆርጅ ገርሽዊን
ፍቅር እንደ ቧንቧ መክፈቻ ነው፤ ይዘጋል ይከፈታል፡፡
ቢሊ ሆሊዴይ
ከፍቅረኛህ ጋር ስትለያይ ጠቅላላ ማንነትህ ይፈራርሳል፡፡ ልክ እንደሞት ማለት ነው፡፡
ዴኒስ ቋይድ
ለሥራ ጊዜ አለው፡፡ ለፍቅር ጊዜ አለው፡፡ ከሁለቱ የሚተርፍ ሌላ ጊዜ የለም፡፡
ኮኮ ቻኔል
በዓለም ላይ ምርጡ ጠረን የምትወጂው ወንድ ነው፡፡
ጄኔፈር አኒስተን
ጀግንነት ሰውን ያለቅድመ ሁኔታ፣ ምላሽ ሳይጠብቁ ማፍቀር ነው፡፡
ማዶና
ፍቅር እንደ ጦርነት ሁሉ ለመጀመር ቀላል፤ ለመጨረስ ግን ከባድ ነው፡፡
ያልታወቀ ሰው
ሦስት ነገሮችን መደበቅ አይቻልም፡- ጉንፋን፣ ድህነትና ፍቅር፡፡
የአይሁዳውያን አባባል
ፍቅር ማለቂያ የሌለው ይቅር ባይነት ነው፡፡
ፒተር ኡስቲኖቭ
ፍቅር ነበልባል የመሆኑን ያህል ብርሃንም መሆን አለበት፡፡
ሔነሪ ዴቪድ ቶሪዮ
ፍቅር የሌላው ሰው ደስታ ለራስህ ወሳኝ የሚሆንበት ሁኔታ ነው፡፡
ሮበርት ሔይንሌይን
ፍቅር ሰውን ከራሱ ባርኔጣ ውስጥ ስቦ የሚያወጣ ምትሃተኛ ነው፡፡
ቤን ሄሽት

Monday, 06 April 2015 08:55

የሲኒማ ጥግ

ሥራውን ሰርተህ ሰዎች እንዲያዩልህ ትፈልጋለህ፡፡ ነገር ግን ሥራውን እየሰራሁ ሳለ ስለውጤቱ አላስብም፡፡ ፊልሙ ተወዳጅ ሆኖ ቦክስ ኦፊስ ቢገባ ወይም ከንቱ ቢሆን ግዴለኝም፡፡ ለእኔ ፊልሙ ተሰርቶ ከተጠናቀቀ በራሱ  ስኬት ነው፡፡ ሁሉም በየራሳቸው መንገድ ስኬት ናቸው፡፡
ጆኒ ዲፕ
የአማካዩ የሆሊውድ ኮከብ ተዋናይ ፍላጎት በአሜሪካዊ መደነቅ፣ በጣሊያናዊ መጠበስ፣ ከእንግሊዛዊ ጋር ትዳር መያዝና ፈረንሳዊ ፍቅረኛ መያዝ ነው፡፡
ካትሪን ሄፕበርን
ለወጣት ፊልም ሰሪዎች የምለግሰው ምክር፡- “ያለውን አካሄድ አትከተሉ፤ አዲስ ጀምሩ!” የሚል ነው፡፡
ፍራንክ ካፕራ
ፊልም ከሦስቱ ዓለም አቀፍ ቋንቋዎች አንዱ ነው፡፡ የቀሩት ሁለቱ ሂሳብና ሙዚቃ ናቸው፡፡
ፍራንክ ካፕራ
ለፊልም ፈተና መሄዴ ነው ብዬ ስናገር መላው ቤተሰቤ ከልቡ ነበር የሳቀው፡፡
ቪክቶሪያ አብሪል
ታላቅ የፊልም ተዋናይ እሆናለሁ፡፡ ይሄ የሚሆነው ግን መጠጥና ወሲብ ካልቀደሙኝ ብቻ ነው፡፡
ጄይ ፕሪሰን አለን
ተዋናይ ከሚሰራበት ፊልም የበለጠ ገዝፎ መታየት የለበትም፡፡
ክርስቲያን ቤል
ፊልምን በተመለከተ ሰዎች ብዙ ጊዜ የመጥፎ ማዕከላዊ ገፀ ባህርይ መልዕክትንና የፊልሙን መልዕክት ብዙ ጊዜ አይለዩትም፡፡ ግን ሁለት የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡
ክርስቲያን ቤል
ሜክሲኮ ያገኘኋት አንዲት ሴት እንድፈውሳት ፈልጋ ነበር፡፡ እኔ ግን ማንንም መፈወስ አልችልም፡፡ እጄን ጭንቅላቷ ላይ አድርጌ፤ “ፊልሙን በማየትሽ አመሰግንሻለሁ” አልኳት፡፡
ጂም ካቪዜል

በኢጋ ሚዲያና ኮሙዩኒኬሽን አዘጋጅነት የሚቀርበው “ሰሙነ ህማማት የስነ ጽሑፍና የበገና ምሽት” የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 11፡30 ሰዓት ጀምሮ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡
በዝግጅቱ ላይ አንጋፋና ወጣት ፀሐፍት፤ ግጥሞችንና ወጐችን በባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያዎች እየታጀቡ ያቀርባሉ ተብሏል፡፡
በምሽቱ ከ20 በላይ የበገና ደርዳሪዎች በአንድ ላይ ተጣምረው በገና በመደርደር ዝግጅቱን እንደሚያደምቁም ተገልጿል፡፡ የዝግጅቱ አላማ ባህላዊ የሙዚቃ መሳሪያና ስነ - ጽሑፍ ያላቸውን ተዛምዶ ለማህበረሰቡ ማስገንዘብና ትኩረት እንዲሰጣቸው ማድረግ ነው ብለዋል - አዘጋጆቹ፡፡  

   ወጋገን ኮሌጅ በፊልም ሙያ ያሰለጠናቸውን ከ130 በላይ አንጋፋና ጀማሪ አርቲስቶች በዛሬው እለት ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ በአለም ሲኒማ አዳራሽ ያስመርቃል፡፡ በምረቃ ስነ ሥርዓቱ ላይ የዩኒቨርስቲ መምህራን፣ ታዋቂ አርቲስቶች እና ጥሪ የተደረገላቸው የመንግስት ባለስልጣናት ይገኛሉ ተብሏል፡፡ የምረቃ ፕሮግራሙን ይታደማሉ ተብሎ ከሚጠበቁ አርቲስቶች መካከል መሰረት መብራቴ፣ ይገረም ደጀኔ፣ ሸዊት ከበደ እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡

Monday, 06 April 2015 08:34

የፖለቲካ ጥግ

ወፍራም ደሞዝ ተከፋይ የአፍሪካ ፕሬዚዳንቶች!!

የደቡብ አፍሪካው ፕሬዚዳንት ጃኮብ ዙማ መደበኛ ትምህርት እንዳልተከታተሉ “አፍሪካ ክራድል” የተባለው ድረገፅ ሰሞኑን ይፋ ያደረገ ሲሆን “7 ቀለም ያልዘለቃቸው የአፍሪካ ፕሬዚዳንቶች” በሚል ባወጣው ዝርዝር ውስጥ ዙማን በአንደኝነት ነው ያስቀመጣቸው፡፡  ሰውየው ያልተማሩ መሆናቸው እምብዛም አልጐዳቸው፡፡ እንደውም ሳይጠቅማቸው አልቀረም፡፡  የዙማ ዓመታዊ ገቢ 270ሺ ዶላር (5ሚ.400ሺ ብር ገደማ) ሲሆን በአሁኑ ሰዓት በአፍሪካ ከፍተኛ ተከፋይ  ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡ ዙማ ከዓለማችን 10 ከፍተኛ (Top 10) ተከፋይ ፕሬዚዳንቶች ውስጥ አንዱ ናቸው፡፡
አልጄሪያን እ.ኤ.አ ከ1999 ጀምሮ በመምራት የአገሪቱ አምስተኛ ፕሬዚዳንት የሆኑት አብደላዚዝ ቡቴፍሊካ ዓመታዊ ደሞዛቸው 168ሺ ዶላር ነው፡፡ ቡቴፍሊካ ሁለተኛው፤ ከፍተኛ ተከፋይ የአፍሪካ ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡
ኡሁሩ ሙይጋይ ኬንያታ አራተኛው የኬንያ ፕሬዚዳንት ሲሆኑ ሥልጣን የተቆናጠጡት እ.ኤ.አ በ2013 ዓ.ም ነበር፡፡ ኬንያታ በዓመት 132ሺ ዶላር ያገኛሉ፡፡ በ2014 ዓ.ም በወር ይከፈላቸው የነበረውን 14ሺ ዶላር ወደ 11ሺ ዶላር እንዲቀነስ በማድረግ አርአያ ለመሆን ሞክረዋል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን ሶስተኛው የአፍሪካ ከፍተኛ ተከፋይ ፕሬዚዳንት ከመሆን ያገዳቸው ነገር የለም፡፡
ኮሞሮስን ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በመምራት ላይ የሚገኙት አይኪሊሎ ዲሆይኒኔ፤ በ115ሺ ዶላር ዓመታዊ ገቢ 4ኛው ከፍተኛ ተከፋይ ፕሬዚዳንት ሆነዋል፡፡ ሰውየው ስልጣን ሲይዙ ሙስናን ከአገሪቱ ለማጥፋት ቃል እንደገቡ ተዘግቧል፡፡ ዲሆይኒኔ ያጠኑት ፋርማሲስትነት ነው፡፡
ዴኒስ ሳሶ ንግዩሶ፤ ከ1997 ዓ.ም ጀምሮ የኮንጎ ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት በመሆን አገሪቱን  እየመሩ ይገኛሉ፡፡ በቅርቡ  “ግሎባል ዊትነስ”  እንደዘገበው፤ የፕሬዚዳንቱ ልጅ ዴኒስ ክሪስትል የአንድ ወር የግል ፍጆታ፣ የ80ሺ የኮንጎ ህፃናትን የኩፍኝ መከላከያ ክትባት ወጪ ይሸፍናል፡፡ የኮንጐው መሪ ዓመታዊ ክፍያ 110ሺ ዶላር ሲሆን 5ኛው ከፍተኛ ተከፋይ የአፍሪካ ፕሬዚዳንት ናቸው፡፡

Monday, 06 April 2015 08:19

የፀሐፍት ጥግ

ከሞትክ በኋላ መረሳት የማትፈለግ ከሆነ አንድም ለመነበብ የሚበቁ ነገሮችን ፃፍ አሊያም ለመፃፍ የሚበቁ ነገሮችን ሥራ፡፡ ቤንጃሚን ፍራንክሊን ተሰጥኦ ብቻውን ፀሐፊ አያደርግም፤ ከመፅሐፉ ጀርባ ሰው መኖር አለበት፡፡ ራልፍ ዋልዶ ኢመርሰን ራሱን የማይመግብ አዕምሮ ራሱን ይበላል፡፡ ጎሬ ቪዳል የመፃፍ ክህሎት፤ ሌሎች ማሰብ የሚችሉበትን ሁኔታ መፍጠር ነው፡፡ ኢድዊን ስክሎስበርግ ድድብና ላለማሰብ ምክንያት አይሆንም፡፡ ስታኒስላው ጄርዚሌክ ብዕር የአዕምሮ ምላስ ነው፡፡ ሰርቫንቴስ ስለችሎታዬ ቅንጣት ታህል ጥርጣሬ ኖሮኝ አያውቅም፡፡ መፃፍ እንደምችል አውቅ ነበር፡፡ እየፃፍኩ እንዴት ሆዴን እንደምሞላ ብቻ ነው ማሰብ የነበረብኝ፡፡ ኮርማክ ማክካርቲ ሰው ብዙ በመፃፍ በወጉ መፃፍ ይለምዳል፡፡ ሮበርት ሳውዜይ ከእያንዳንዱ የሰባ መፅሃፍ ውስጥ ለመውጣት የሚፍጨረጨር ቀጭን መፅሃፍ አለ፡፡ ያልታወቀ ፀሐፊ ፀሐፊ ይመሰገን እንደሆነ ለማየት ሌላ የህይወት ዘመን ያስፈልገዋል፡፡ ጆርጅ ሉዊስ ቦርግስ ለራስህ በጣም ቀሽም ፅሑፍ የመፃፍ ዕድል ካልሰጠኸው በጣም ግሩም ፅሁፍ ለመፃፍ ትቸገራለህ፡፡ ስቲቨን ጋሎዌይ አንባቢውን ማሰልቸት ይቅር የማይባል ሃጢያት ነው፡፡ ላሪ ኒቬን

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ባላገር አንድ የማያውቀው ጫካ አቋርጦ ወደ መንገዱ ሊወጣ ሲጓዝ፤ አንድ የንጉሥ ልጅ በፈረስ ሆኖ ሲንሸራሸር ባላገሩን ያገኘዋል፡፡ ባላገሩ እጅ አልነሳም ልዑሉን፡፡ አልተሸቆጠቆጠም፡፡
ልዑሉ በጣም ገረመው፡፡ በአገሩ ደንብ ንጉሥን አክብሮ ለጥ ብሎ እጅ መንሳት ነበረበት፡፡ ባያውቅ ነው ብሎ በመገመት፤
“እንደምን ዋልክ?” ይለዋል፡፡
“ደህና እግዚሐር ይመስገን” ይላል ባላገሩ፡፡
“ለመሆኑ ንጉሥ ማለት ምን ማለት እንደሆነ ታውቃለህ?”
“አላውቅም” አለ ባላገር፡፡
“እንግዲያው ና ፈረሴ ላይ ውጣ፡፡ አፈናጥጬ ይዤህ እሄዳለሁ፡፡ ንጉሥ ማለት በሄደበት ሁሉ ሰው እጅ የሚነሳው፣ መንገደኛ ቆሞ የሚያሳልፈው የተከበረ ሰው ነው። ስለዚህ ቀስ በቀስ ንጉሥ ምንና ማን እንደሆነ ይገባሃል” አለና ያን ባላገር አፈናጠጠው፡፡
ወደ ከተማ እየተቃረቡ መጡ፡፡
“እንግዲህ አሁን ልብ ብለህ አስተውል” አለ ልዑሉ፡፡
የከተማው ሰው ልዑሉን ሲያይ ወዲያው የሚሄደው ቆመ፡፡ የቆመው ለጥ እያለ እጅ ነሳ፡፡ ልዑል  ዝም ብሎ መንገዱን ይቀጥላል፡፡ ህዝም እየቆመ እጅ እየነሳ ማሳለፉን ቀጥሏል፡፡ ይሄኔ ልዑሉ፡-
“አንተ ባላገር፤ ንጉሥ ማን እንደሆነ አሁን ገባህ?” ሲል የጠቀው፡፡
ባላገሩም፤
“አዎን አሁን ገብቶኛል” አለ፡፡
ልዑሉ ቀጥሎ፤
“ማን ነው ንጉሡ?” አለና ጠየቀ፡፡
ባላገሩም፤  
“እንግዲህ ወይ እኔ ወይ አንተ ነና!” አለና መለሰ፡፡
*       *      *
ስለተፈናጠጡ ብቻ የነገሡ የሚመስላቸው አያሌ አይተናል፡፡ በተሰጣቸው ትርጓሜ - ነገር (Definition) መሠረት ብቻ ጉዳዮችን እየተረጎሙ የሚጓዙ የዋሃንንም አስተውለናል፡፡ ግራ ቀኙን ሳያዩ በተሰመረው መስመር ላይ ብቻ የሚነጉዱ፣ ወቅት የሚለወጥ የማይመስላቸውና ወቅትም የማይለውጣቸው በርካታ መንገዶችን ታዝበናል፡ “ሳይማር ያስተማረንን ገበሬ አንረሳውም” ብለው ሲያበቁ ከተማ ገብተው ከተሜ ሲሆኑ፤ የሚገነቡትን ህንፃ ብቻ ዐይን ዐይኑን እያዩ መሰረታቸውን የረሱ ዕልቆ መሣፍርት የሌላቸው መሆናቸውንም ገርሞን አይተናል፡፡ ጥንት “ሠፊው የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ! የረሱህን አልረሳናቸውም” ብለው ጀምረው ከነመፈጠሩም ያላስታወሱት ባለጊዜዎችንም ተመልክተናል፡፡ በህዝብ የሚምል የሚገዘት ፓርቲ፣ ድርጅት፣ ማህበር አገራችን አጥታ አታውቅም!
የፖለቲካ አየር የኢኮኖሚውን ንፋስ መከተሉ በዓለም ታሪክ እንግዳ ነገር አይደለም። የኢኮኖሚ ብሶት ወደ ፖለቲካ ምሬት መለወጡና የፖለቲካ ጥያቄን መውለዱም ሁለንተናዊ ዕውነታ ነው፡፡ ይሄ የቆረቆረው ፓርቲ፣ ድርጅት፣ ቡድን ወዘተ… ጥያቄውን አንግቦ መነሳቱና መልስ መሻቱ አይቀሬ ነው፡፡
ከጭፍን ጥላቻ ውጪ ይሄን ጥያቄ ማንሳት ዲሞክራሲያዊ መብት ነው፡፡ መብቱን የሚያውቅ፣ የገባውና የሚገባውን የሚያውቅ ዜጋ ያላት አገር የታደለች ናት! ይህንን ዕድል ለመጠቀም የሚችል ንቃተ ህሊናው የበለፀገ ዜጋ ሀገሩን በቅጡ ይታደጋታል ተብሎ ይገመታል፡፡ እንዲህ ያለ ዜጋ የገዛ ዐይኑን ጉድፍ ሳያነፃ ከወንድሙ ዓይን ጉድፍ አወጣለሁ ብሎ አይፍረመረምም፡፡ ራሱን ከሙስና አያድንምያላፀዳ ዜጋ፤ አገሩን ከሙስና አያድንም፡
ራሱን ዲሞክራሲያዊና ፍትሐዊ ያላደረገ ታጋይ፤ ዴሞክራሲያዊና ፍትሐዊ ሥርዓትን እገነባለሁ ቢል ሐሳዊ ታጋይ ከመሆን አያልፍም፡፡ ራሱ ህገ - ወጥ የሆነ ኃላፊ፤ የህግ የበላይነትን ያስከብራል ብሎ ተስፋ ማድረግ ከእባብ ዕንቁላል እርግብ መጠበቅ ነው፡፡
የምርጫ ወቅት ላይ ብቻ ስለ ኢ-ወገናዊነት የሚሰብክ ሰሞነኛ ወይም የወረት መንገደኛ ፍሬው በቀላሉ አይጐመራም፡፡ ጧት የተነሳ ብቻ ነው የማታ አዝመራው የሚሰምርለት፡፡
ፀሐፍት እንደሚሉት፤
“የምርጫ ወቅት ሙስና፡- Fake የይስሙላ ፓርቲዎችን ተወዳዳሪ አስመስሎ ከማቅረብ፣ እስከ ድምጽ ስርቆት ሊሄድ ይችላል፡፡
“በዚህ ምክንያት ነው በብዙ የአፍሪካ አገሮች ምርጫ ከመነሻው እስከ መድረሻው በውዝግብ የታጀበ የሚሆነው!”
ይሄን ልብ ብሎ ያልተገነዘበ ዜጋ ቡድን፣ ድርጅት ለራሱም አይሆን፤ ለአገሩም አይበጅ፡ ይልቁንም ነቅቶ መጠበቅ፤ ድምፁን እንዳያጣ፣ እንዳይጭበረበር፣ ያግዘዋል፡፡ ያ ካልሆነ ህዝባዊ ገዥነቱን የሚያረጋግጥበትን ዋና አቅሙን፣ ሠረገላ ቁልፉን አጣ ማለት ነው፡፡ የሚከበርና የሚፈራ ህዝብ የሚኖረው መብቱን የሚያውቅና የሚያስከብር ሆኖ ሲገኝ ነው፡፡ መብቱን ሲሸራርፉበት እምቢ! ማለት ሲችል ነው፡፡ በደልን፣ ግፍን እያየ ዝም ሳይል ሲቀር ነው፡፡ የፖለቲካ ሙስናን አልቀበልም ማለት ሲችል ነው፡፡ አስተዳደራዊ ብልሹነትን አሻፈረኝ ማለት ሲችል ነው! ቢሮክራሲያዊ እንቅፋቶችን አልቀበልም ማለት ሲችል ነወ፡፡ ባላስደሰተኝ ነገር አላጨበጭብም ማለት ሲችል ነው፡፡ እስከዛሬ ባየናቸው የተቃውሞ ጉዞዎች ውስጥ አማራጭ የትግል ስልቶችን ሳይቀይሱ በአንድና አንድ ግትር ስልት ብቻ እንጓዝ ብለው ብቸኛ መንገድ የመረጡ ሰዎች ቢያንስ መጨረሻቸው አያምርም፡፡ ሁለተኛም ሶስተኛም መጓዣ መንገዶችን ገና በጠዋት ማዘጋጀት ይገባቸዋል፡፡ ፈረንጆቹ “ፕላን ቢ”፣ “ፕላን ሲ” እንደሚሉት ነው፡፡ በአማርኛ “ሁለት ባላ ትከል፤ አንዱ ቢሰበር ባንዱ ተንጠልጠል” እንደማለት ነው!